Administrator

Administrator

    በአለም ባንክ እና በሌሎች አለማቀፍ ተቋማት የገንዘብ ድጋፍ በኢትዮጵያ ውስጥ በሚከናወኑ ፕሮጀክቶች የሰብዓዊ መብት ጥሰቶች እየተፈጸሙ ነው በሚል የባንኩ የውስጥ መርማሪ ቡድን ያወጣውን ሪፖርት ባንኩ በትኩረት ተመልክቶ ተገቢውን ምላሽ እንዲሰጠው ሂውማን ራይትስ ዎች ጠየቀ፡፡
ባንኩ በበኩሉ፤ መርማሪ ቡድኑ ባወጣው ሪፖርት ላይ የተጠቀሱ ለሰብአዊ መብት ጥሰቶች በር የሚከፍቱ በርካታ የአሰራር ችግሮች እንደሌሉበት ገልጾ፣ ጥናቱ እንደገና ሊከለስ ይገባል ብሏል፡፡ የአለም ባንክ የዳይሬክተሮች ቦርድ የመርማሪ ቡድኑን ሪፖርት ለመገምገምና የማኔጅመንቱን ምላሽ ለማሰማት በትናንትናው ዕለት ስብሰባ አድርጓል፡፡
ሂውማን ራይትስ ዎች ለአለም ባንክ የአፍሪካ ምክትል ፕሬዚደንት በላከው ደብዳቤ እንዳለው፣ የባንኩ ገለልተኛ የተጠያቂነት ስልት መርማሪ ቡድን በጉዳዩ ዙሪያ ባደረገው ምርመራ በኢትዮጵያ በሚከናወኑ ፕሮጀክቶች ላይ ተግባራዊ የሚያደርገውን የራሱን ፖሊሲ እንደሚጥስ ማረጋገጡን አስታውቋል፡፡
ቡድኑ ባለፈው ወር ባወጣው ሪፖርት፤ በአለም ባንክ ፕሮጀክቶችና በኢትዮጵያ መንግስት የመልሶ ማስፈር ፕሮግራም መካከል የአሰራር ግንኙነት እንዳለ ማረጋገጡንና ይህም የአለም ባንክ ለነባር ህዝቦች መብቶች መከበር የቆመውን የራሱን ፖሊሲ እየጣሰ እንደሚገኝ የሚያረጋግጥ እንደሆነ ማስታወቁንም አክሎ ገልጧል፡፡
መርማሪ ቡድኑ መሰረታዊ አገልግሎቶችን የማስፋፋት ዓላማ ያላቸውንና በአለም ባንክ፣ በእንግሊዝ መንግስት የአለማቀፍ ልማት ድርጅት፣ በአፍሪካ ልማት ባንክ እና በሌሎች ለጋሾች የገንዘብ ድጋፍ የሚደረግላቸውን ፕሮጀክቶች በተመለከተ ከጋምቤላ ክልል ስደተኞች የቀረበለትን ቅሬታ መነሻ በማድረግ ባደረገው ማጣራት፣ የአለም ባንክ በፕሮጀክቶቹ ውስጥ ለሚታዩ የሰብአዊ መብት ጥሰት አደጋዎች ይህ ነው የሚባል ትኩረት እንዳልሰጠ ማረጋገጡን የሂውማን ራይትስ ዎች አለማቀፍ የገንዘብ ተቋማት ከፍተኛ ተመራማሪ የሆኑት ጀሲካ ኢቫንስ ገልጸዋል፡፡
የአለም ባንክ በኢትዮጵያ የሚያከናውናቸውን ፕሮጀክቶች አካሄድ ማስተካከል የሚችልበት ዕድል አለ ያሉት ጀሲካ ኢቫንስ፣ ባንኩ የሰብዓዊ መብት ጥሰቶች ሰለባ የሆኑ ስደተኞችን የመብቶቻቸው ተጠቃሚ የማድረግ ሃላፊነት እንዳለበትም ገልጸዋል፡
ኢትዮጵያ የሚሊኒየሙን የልማት ግቦች በማሳካት ረገድ አበረታች ውጤት ማስመዝገቧ፣ አገሪቱ ጠንካራ የኢኮኖሚ እና የአገር ውስጥ ገቢ እድገት እያሳየች መሆኗን ያመላክታል ያለው የእንግሊዝ መንግስት በበኩሉ፣ ይህም የአገሪቱን ፍላጎት ባገናዘበ መልኩ የሚሰጠውን እርዳታ ከመሰረታዊ የሰብዓዊ እርዳታ ወደ ስራ ፈጠራና ራስን የሚያስችሉ ፕሮጀክቶች ለማዞር እንዳነሳሳው ከትናንት በስቲያ አስታውቋል፡፡ የእግሊዝ መንግስት የእርዳታ አቅጣጫ ለውጡ ለኢትዮጵያ በሚሰጠው የገንዘብ መጠን ላይ ተጽዕኖ እንደማያሳድርና በኢትዮጵያ ድህነትን ለመቀነስ በሚደረጉ ጥረቶች ውስጥ አጋርነቱን አጠናክሮ እንደሚቀጥል መግለጹን ተከትሎ፣ የኢትዮጵያ መንግስትም ለእንግሊዝ መንግስት ያለውን አድናቆት ገልጿል፡፡

*በርካታ የውጭ ዩኒቨርሲቲዎች ይሳተፉበታል

ሜድኮ ባዮ ሜዲካል ኮሌጅ የፊታችን ሰኞና ማክሰኞ ትምህርታዊ ፌስቲቫል ያካሄዳል፡፡ “የትምህርት እድልን በተቀናጀ መንገድ ከውጭ ዩኒቨርሲቲዎች ጋር ተማሪዎችን ማገናኘት” በሚል መሪ ቃል በሜድኮ ባዮ ሜዲካል ኮሌጅ ውስጥ በሚካሄደው ትምህርታዊ ፌስቲቫል ላይ በርካታ የውጭ ዩኒቨርስቲዎች እንደሚሳተፉ የተገለጸ ሲሆን ከነዚህም ውስጥ የአሜሪካው ካሊፎርኒያ ዩኒቨርሲቲና ፍራንክሊን ዩኒቨርሲቲ፣ የህንዱ አቻርያ ኢንስቲቲዩት፣የቱርኩ ኦካን ዩኒቨርሲቲ፣ የካናዳው ብሮንስቶን አካዳሚ፣ የማሌዢያው ማሌዢያ የትምህርት ማዕከል፣ የጣሊያኑ ካቶሊካ ዩኒቨርሲቲ፣ የኡጋንዳው ቪክቶሪያ ዩኒቨርሲቲ፣ የስዊዘርላንዱ ሆቴልና ቱሪዝም ማኔጅመንት ኢንስቲትዩት፣ የቆጵሮሱ ግሪኒ አሜሪካን ዩኒቨርሲቲ፣ የደቡብ አፍሪካው ጆሀንስበርግ ዩኒቨርሲቲና ሌሎችም ዩኒቨርሲቲዎች እንደሚገኙበት የኮሌጁ የሚዲያ አስተባባሪ አቶ ቶፊቅ ሁሴን ገልጸዋል፡፡
በሜድኮ ባዮ ሜዲካል ኮሌጅ አስተባባሪነት ለመጀመሪያ ጊዜ የሚካሄደው ትምህርታዊ ፌስቲቫል ቀጣይነት እንደሚኖረው የተገለጸ ሲሆን የሌሎች አገራት ዩኒቨርሲቲዎችም በየተራ ፌስቲቫሉን ያዘጋጃሉ ተብሏል፡፡ የፌስቲቫሉ ዋና ዓላማ ዓለም አቀፍ ዩኒቨርሲቲዎችና ተማሪዎችን በማገናኘት ልምድ ማለዋወጥና በስኮላርሺፕ ሂደት ላይ ደላሎች የሚሰሩትን አሻጥር በማስቀረት፣ የየአገራቱ ዩኒቨርሲቲዎች በትምህርታቸው ብልጫ ላላቸው ተማሪዎች በቀጥታ የትምህርት እድል እንዲሰጡ ለማድረግ እንደሆነ አቶ ቶፊቅ ተናግረዋል፡፡  
የፊታችን ሰኞና ማክሰኞ ከጠዋቱ ሶስት ሰዓት እስከ 11 ሰዓት በሚካሄደው ፌስቲቫል፤የአገራችንም ዩኒቨርሲቲዎች የሚሳተፉ ሲሆን ፌስቲቫሉ አገራችን ለትምህርት ጥራትና ተደራሽነት የምታደርገውን ጥረት በማገዝ በእውቀት የበለፀገ ማህበረሰብን ለማፍራት ቁልፍ ሚና ይኖረዋል ተብሏል፡፡ በዚህ ፌስቲቫል ላይ የልምድ ልውውጦች፣ የፓናል ውይይቶችና መሰል ዝግጅቶች የሚካሄዱ ሲሆን የከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ተማሪዎች፣ መምህራንና ጉዳዩ የሚመለከታቸው አካላት በስፍራው ተገኝተው እንዲጎበኙት ሜድኮ ባዮ ሜዲካል ኮሌጅ ጋብዟል፡፡

በአስር አመት ውስጥ የኢኮኖሚ አቅማቸው ደካማ ለሆኑ 800 ወንድና ሴት ተማሪዎች የነፃ ትምህርት ዕድል የሚያስገኘው የማስተር ካርድ ስኮላር ፕሮግራም ትናንት በይፋ ተጀመረ፡፡ በ100 ወጣት ወንድና ሴት ተማሪዎች የተጀመረው የነፃ ትምህርት ዕድል፤ከዘጠነኛ እስከ አስራ ሁለተኛ ክፍል ድረስ ትምህርታቸውን ለሚከታተሉ  ተማሪዎች ድጋፍ ያደርጋል፡፡ የኢኮኖሚ አቅማቸው ደካማ ሆኖ ጥሩ የትምህርት ፍላጐት ያላቸውንና ጐበዝ ተማሪዎችን ከአማራ፣ ከኦሮሚያ፣ ከደቡብ ክልሎችና ከአዲስ አበባ አስተዳደር በማሰባሰብ የነፃ ትምህርት ዕድሉ ተጠቃሚ እንዲሆኑ የተደረገው ተብሏል፡፡  
Forum for African women education (FAWE) በተባለው ድርጅት በተጀመረው የነጻ ትምህርት እድል ፕሮጀክት በአስር ዓመት ውስጥ ተጠቃሚ የሚሆኑት 800 ወጣቶች ሲሆኑ 600 ያህሉ ሴት ተማሪዎች ናቸው፡፡ በትምህርታቸው የላቀ ውጤት የሚያስመዘግቡ ተማሪዎች በውጭ አገር ነጻ የከፍተኛ ትምህርት ዕድል ሊያጋጥማቸው እንደሚችልም ተገልጿል፡፡

- ከመደበኛው 218 ሚ ዶላር መሸጫ ዋጋቸው በግማሽ ቅናሽ እንደሚሸጡ ይጠበቃል
 
ቦይንግ ኩባንያ ቀደም ባለ ሞዴል ካመረታቸው የመጨረሻዎቹ ቦይንግ 787 - 8 ድሪምላይነር አውሮፕላኖችን ውስጥ ስምንቱን ለኢትዮጵያ አየር መንገድ ለመሸጥ ድርድር እያደረገ መሆኑን ብሉምበርግ ኒውስ ዘገበ፡፡
ኩባንያው አውሮፕላኖቹን ለእያንዳንዳቸው ከተመነላቸው የ218 ሚሊዮን የአሜሪካ ዶላር መደበኛ የመሸጫ ዋጋ ላይ በግማሽ ያህል ቅናሽ አድርጎ ይሸጣቸዋል ተብሎ እንደሚጠበቅ የጠቆመው ዘገባው፣ አውሮፕላኖቹን ለመግዛት ከኩባንያው ጋር ድርድር ከጀመሩት አየር መንገዶች መካከል፣ የኢትዮጵያ አየር መንገድ የተሸለ ድርድር በማድረግ ወደ መጨረሻው ምዕራፍ መዳረሱን አስታውቋል፡፡
ከዚህ ቀደም ተመሳሳይ አውሮፕላኖችን ከኩባንያው የገዙ ደንበኞች በዚህኛው ግዢ ላይ ለመሳተፍ አለመፈለጋቸውን የጠቆመው ዘገባው፣ ለዚህም በምክንያትነት የተጠቀሰው የአውሮፕላኖቹ ክብደት በጣም ከፍተኛ ከመሆኑን ጋር ተያይዞ የሚሸፍኑት የበረራ ክልል ውስን መሆኑ እንደሆነ ገልጧል፡፡
ቦይንግ በሚያመርታቸው ድሪምላይነር አውሮፐሮላኖች ከዚህ ቀደም ባደረጓቸው የሙከራ በረራዎች፣ የተለያዩ ቴክኒካዊና የዲዛይን ችግሮች እንዳሉባቸው መረጋገጡን ተከትሎ፣ ቦይንግ ኩባንያ በአውሮፕላኖቹ ዲዛይንና አሰራር ላይ ለውጥ ለማድረግ ተገድዶ እንደነበርም ዘገባው ጨምሮ አስታውሷል፡፡


ለብዙ የአዲስ አበባ ነዋሪ አማራጭ እንደሆኑ በጥናት ሪፖርት ተገልጿል
በአዲስ አበባ የሚገኙ የጤና ተቋማት የሚሰጡት አገልግሎት በአመዛኙ በመንግስት ስር ካሉት ተቋማት የተሻለ ቢሆንም፣ ግማሽ ያህሉ ገና ከደረጃ በታች እንደሆኑ ተገለፀ፡፡ በመንግስትና በግል ጤና ተቋማት ያለው የክፍያ ልዩነት ከአራት እስከ አርባ እጥፍ ይደርሳል፡፡
የግል ህክምና ተቋማት በአዲስ አበባ የሚሰጡት አገልግሎት ላይ ጥናት የተካሄደው በ“ማህበራዊ ጥናት መድረክ” አማካኝነት ሲሆን፣ ትናንት ይፋ የሆነው የጥናት ሪፖርት ከአገልግሎት ጥራት በተጨማሪ የክፍያ መጠኖችንም በማነፃፀር ዳስሷል፡፡ የግል የጤና ተቋማቱ ከመንግስት የጤና ተቋማት ጋር ሲነጻጸሩ የተሻለ ደረጃ ላይ እንደሚገኙ የጥናት ሪፖርቱ ጠቅሶ፤ ይህ ማለት ግን የአገልግሎት ደረጃን ያሟላሉ ማለት እንዳልሆነ ገልጿል፡፡
አዳዲስ ሆስፒታሎችና ክሊኒኮች የስራ ፈቃድ የሚያገኙት በቅርቡ እንደ አዲስ በተዘጋጀው የጥራትና ደረጃ መስፈርት እንደሆነ በጥናቱ የተገለፀ ሲሆን በመስፈርቱ መሰረትም 34 የግል ሆስፒታሎች ላይ ዝርዝር ጥናት ተካሂዷል፡፡ የጥናቱ ሪፖርት እንደሚገልፀው፤ የጥራት ደረጃ መስፈርቶችን በአግባቡ ያሟላሉ ሆስፒታሎች ከሁለት አይበልጡም፡፡ 17 ያህል ሆስፒታሎች (ማለትም 50% ያህሉ) በመካከለኛ ሁኔታ ላይ እንደሆኑና ማሻሻያ እንደሚያስፈልጋቸው ጥናቱ ገልፆ፤ 15 ያህል ሆስፒታሎች ግን በዝቅተኛ ደረጃ ላይ የሚገኙ ናቸው ብሏል፡፡
 ባለፉት አምስት አመታት የግል የህክምና ተቋማት እድገት ማሳየታቸውን ያመለከተው ጥናቱ፤ 42 በመቶ ለሚሆነው የከተማዋ ነዋሪ አገልግሎት እየሰጡ እንደሆነና አገልግሎታቸው ለከተማው ሀብታሞች ብቻ ሳይሆን በዝቅተኛ ገቢ ለሚተዳደሩ ነዋሪዎችም ጭምር እንደሚደርስ ገልጿል፡፡
ጥናቱ የአገልግሎት ክፍያን በተመለከተ የግል የጤና ተቋማት ከሚሰጡት የአገልግሎት ጥራት ጋር ያልተመጣጠነ ከፍተኛ ክፍያ እንደሚጠይቁ አመልክቷል፡፡ በተለይ ከመንግስት የጤና ተቋማት ጋር ሲነጻጸር ክፍያው የትየለሌ መሆኑን የጠቆመው ጥናቱ፤ ለምሳሌ በኤክስሬይ የዋጋ ልዩነቱ 40 እጥፍ ገደማ ሲሆን በወሊድ አገልግሎትም በተመሳሳይ የክፍያ ልዩነቱ ወደ 40 እጥፍ ይጠጋል፡፡
በእርግጥ የግልና የመንግስት የጤና ተቋማት ክፍያ ተቀራራቢ ይሆናል ተብሎ የሚጠበቅ አይደለም፡፡ የመንግስት የጤና ተቋማት ስራቸውን የሚያከናውኑት ከክፍያ በሚያገኙት ገንዘብ ብቻ ሳይሆን ከታክስ ከሚሰበሰብ ገንዘብና ከውጭ ከሚመጣ እርዳታ በጀት እተመአበላቸው እንደሆነ ይታወቃል፡፡  

የአገልግሎት አይነት    የግል ሆስፒታል ክፍያ በአማካይ    የጤና ጣቢያ ክፍያ በአማካይ
የካርድ                        100           5
ኤክስሬይ                      180          35
በምጥ ማዋለድ               1940           50
በኦፕራሲዮን ማዋለድ         3550         140
የወንዶች ግርዛት                520          35
ትርፍ አንጀት ቀዶ ህክምና    2850          120
የአልጋ አንደኛ ደረጃ            850          90
የአልጋ ሶስተኛ ደረጃ           350          20

በግል የጤና ተቋማት ውስጥ እንደ ችግር ከተጠቀሱት መካከል ለባለሙያዎች ማበረታቻና ተከታታይ ስልጠና አለመሰጠቱ፣ በህክምና ዘርፍ የሚሰማሩ ባለሃብቶች የመሥሪያ መሬት ለማግኘት መቸገራቸው፣ የባለሙያዎች እጥረት፣ የብድር እጦት፣ የጉምሩክ ቢሮክራሲና የውጭ ምንዛሬ እጥረት ይገኙባቸዋል፡፡  





119ኛውን የአድዋን የድል በዓል ለማክበር ጥር 15 ቀን 2007 ወደ አድዋ የእግር ጉዞ የጀመሩት ስድስቱ ተጓዦች ዛሬ “እንዳአባ ገሪማ” የሚባል ቦታ በሰላም መድረሳቸው ታውቋል፡፡
ሲሳይ ወንድሙ፤ መኮንን ሞገሴ፣ ጽዮን ወልዱ፣ ግደይ ስዩም፣ ታምሩ አሸናፊና አዳነ ከማል የተሰኙት እኒህ ተጓዣች እስካሁን በጉዟቸው ምንም ችግር እንዳልገጠማቸውና ሴቷም ተጓዥ ብትሆን በጉዞዋ ከወንዶቹ እኩል መቀጠል እንደቻለች ምንጮች ጠቅሰዋል፡፡ በነገው እለት አድዋ ገብተው የሶሎዳን ተራራ ግማሽ ያህሉን ወጥተው ያድራሉ የተባሉት ተጓዦቹ ሰኞ በማለዳ ተነስተው ወደ ሶሎዳ ተራራ ጫፍ በመውጣት ባንዲራ ከሰቀሉ በኋላ ተራራውን ወርደው አድዋ ከተማ ውስጥ የሚከበረውን የአድዋ 119ኛ በዓል እንደሚታደሙ ታውቋል፡፡ አምና 118ኛውን የአድዋ በዓል ለመታደም አምስት ተጓዦች ለ40 ቀናት በእግራቸው ተጉዘው አድዋ መድረሳቸው የሚታወስ ሲሆን የዘንድሮውን ጉዞ ሴት ተጓዥ መቀላቀሏ ለየት ያደርገዋል ተብሏል፡፡

“ ሲአይኤና ሞሳድ አይሲስ እና ቦኮ ሃራምን ይደግፋሉ” አልበሽር
“ አይሲስን ለመዋጋት የጦር መሳሪያ ማዕቀብ ይነሳልኝ” ሊቢያ

ፕሬዚዳንት ባራክ ኦባማ፤ አይሲስ የተባለውን እስላማዊ ቡድን ጨምሮ ሌሎች ጽንፈኛ ቡድኖች በተለያዩ አገራት የሚፈጽሙትን የሽብር ተግባር ለመግታት የአለም አገራት ተባብረው እንዲሰሩ ጥሪ አቀረቡ፡፡
ኒውዮርክ ታይምስ እንደዘገበው፤ የ60 አገራት ተወካዮች በተገኙበትና በዋሽንግተን በተካሄደው በጽንፈኝነት ላይ ያተኮረ ስብሰባ ላይ ባለፈው ረቡዕ ንግግር ያደረጉት ፕሬዚዳንት ባራክ ኦባማ፣ የአለም አገራት መንግስታት የእስላማዊ መንግስት መርህን አንግበው የሚንቀሳቀሱ ጽንፈኛ ቡድኖችን በተባበረ ክንድ መመከት ይገባቸዋል ብለዋል፡፡
የሱኒ ታጣቂ ቡድኖችን አስተሳሰብ ማዳከምና እንቅስቃሴያቸውን መግታት የትውልድ ፈተና ሆኖ ቆይቷል ያሉት ኦባማ፤ ቡድኖቹን በስኬታማ መንገድ ከእንቅስቃሴያቸው መግታት የሚቻለው በእስልምና እምነት ተከታዮች፣ በመንግስታት፣ በሃይማኖት መሪዎች፣ በማህበረሰቦችና በመሳሰሉት የተቀናጀ ርብርብ ብቻ ነው ብለዋል፡፡
ኦባማ አሜሪካ ጦርነት ውስጥ የገባችው ከእስልምና ጋር ሳይሆን የእስልምናን አስተምህሮት ከሚያዛቡ የጥፋት ሃይሎች ጋር ነው ማለታቸውን የዘገበው ሮይተርስ፤ እስላማዊ ታጣቂ ቡድኖች ምዕራባውያን በእስልምና ላይ ጦርነት አውጀዋል በማለት የሚያቀርቡትን ውንጀላ መሰረተ ቢስ ነው ሲሉ ማጣጣላቸውን ጠቁሟል፡፡ አሜሪካም እና ሌሎች ምዕራባውያን አገራት እስልምናን ለመጨቆንና በእምነቱ ላይ ጥላቻ እንዲስፋፋ ለማድረግ ይሰራሉ በሚል ከአንዳንድ አክራሪ ቡድኖች የሚሰነዘረውን ውንጀላ መሰረተ ቢስነት ለማረጋገጥ የእስልምና መሪዎች ጠንክረው መስራት ይገባቸዋል ብለዋል ኦባማ፡፡
አለማችን ከእስልምና አስተምህሮት ጋር ጸብ የላትም፣ አይሲስ እና አልቃይዳን የመሳሰሉ ቡድኖች ግን የሃይማኖት መሪዎች ሳይሆኑ በሃይማኖት ሽፋን ጥፋት የሚፈጽሙ  ሽብርተኞች ስለሆኑ እንታገላቸዋለን ማለታቸውንም ቢቢሲ ዘግቧል፡፡
የተባበሩት መንግስታት ድርጅት በጠራው አስቸኳይ ስብሰባ ላይ የተሳተፈችው ሊቢያ በበኩሏ፤ አይሲስን እና ሌሎች ጽንፈኛ ታጣቂ ቡድኖችን በአግባቡ ለመመከት እንድትችል፣ የተመድ የጸጥታ ምክር ቤት የጣለባትን የጦር መሳሪያ ግዢ ማዕቀብ እንዲያነሳላት ጠይቃለች፡፡ ማዕቀቡ ከአራት አመታት በፊት እንደተጣለባት ያስታወሱት የሊቢያ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ሞሃመድ አል ዳሪ፤ በአገሪቱ ያለው የጸጥታ ሁኔታ አሳሳቢ ደረጃ ላይ መድረሱን ጠቅሰው  የአገሪቱ ታጣቂ ቡድኖች ከአይሲስ ጋር ተባብረው የባሰ ጥፋት ሊፈጽሙ እንደሚችሉ ስጋታቸውን ገልጸዋል፡፡ ለዚህም በቂ የጦር መሳሪያ መያዟ ወሳኝ እንደሆነ ጠቁመዋል፡፡
በቅርቡ  21 ዜጎቿ በአይሲስ ታጣቂዎች ተቀልተው የተገደሉባትና በቡድኑ ላይ የአየር  ላይ የአጸፋ ምላሽ የሰነዘረችው ግብጽ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ሳሜህ ሽኩርም፣ በሊቢያ ያለው የጽንፈኛ ቡድኖች እንቅስቃሴ ከፍተኛ ችግር የሚፈጥር በመሆኑ፣ በአገሪቱ ላይ የተጣለው የጦር መሳሪያ ግዢ ማዕቀብ መነሳቱ ጠቃሚ እንደሆነ ጠቁመው  ሃሳቡን እንደሚደግፉት ገልጸዋል፡፡
የሱዳኑ ፕሬዚዳንት ኦማር ሃሰን አልበሽር በበኩላቸው፤ የአሜሪካና የእስራኤል የስለላ ተቋማት ሲአይኤና ሞሳድ ለአሸባሪዎቹ እስላማዊ ቡድኖች አይሲስ እና ቦኮ ሃራም በስውር ድጋፍ ይሰጣሉ ሲሉ መወንጀላቸውን  ዘ ኢንዲፔንደንት ዘግቧል፡፡
አይሲስ ከቀናት በፊት በሊቢያ የኮፕቲክ ክርስቲያን አማኝ የሆኑ 21 ግብጻያውንን በመቅላት መግደሉን ተከትሎ ፕሬዚዳንቱ ከዩሮኒውስ ጋር ባደረጉት ቃለመጠይቅ እንዳሉት፣ ይህን መሰሉን የጭካኔ ተግባር የሚፈጽም የእስልምና እምነት ተከታይ የለም፣ ይልቁንም ለዚህ ቡድን የጭካኔ ተግባር ድጋፍ የሚያደርጉት  ሁለቱ የስለላ ተቋማት ናቸው ብለዋል፡፡
መሰል የአሸባሪ ቡድኖችን ለመደምሰስ ሲባል የሚፈጸም ሃይል የተሞላበት እርምጃም ቡድኖቹ የከፋ የአጸፋ ምላሽ እንዲሰጡ የሚገፋፋ ሊሆን ይችላል ሲሉም አልበሽር አስጠንቅቀዋል፡፡ የሊባኖሱ ሂዝቦላህ መሪም ሲአይኤ እና ሞሳድ ከጽንፈኞቹ ቡድኖች በስተጀርባ ድጋፍ ያደርጋሉ ሲሉ መወንጀላቸውን አሶሼትድ ፕሬስ መዘገቡ ተጠቁሟል፡፡
የቱርኳ አንካራ ከተማ ከንቲባ ሜሊህ ጎኬክ በበኩላቸው፤ ሞሳድ በፓሪሱ የቻርሌ ሄቢዶ ጥቃት ውስጥ ተሳትፎ ነበረው ሲሉ መናገራቸውን ባለፈው ጥር ወር ለንባብ የበቃው ፋይናንሽያል ታይምስ ማስነበቡንም ዘገባው አስታውሷል፡፡ ከንቲባው በወቅቱ እንዳሉት፤ እስራኤል በእስልምና ሃይማኖት ላይ ጥላቻ እንዲነግስ በማሰብ ጥቃቱን በማቀነባበር ተሳትፎ አድርጋለች፡፡ በተደጋጋሚ አሰቃቂ ግድያዎችን መፈጸሙን አጠናክሮ የቀጠለው አይሲስ በያዝነው ሳምንትም፣ በ21 ግብጻውያን ላይ ከፈጸመው አንገት የመቅላት ግድያ በተጨማሪ በኢራቋ ከተማ አል ባግዳዲ 45 ሰዎችን በእሳት አቃጥሎ መግደሉ ተዘግቧል፡፡


በታሪክ ከፍተኛው ዝርፊያ ነው ተብሏል

የሩስያ፣ ዩክሬን፣ቻይና እና የአውሮፓ አገራት ዜግነት ያላቸው የኢንተርኔት አጭበርባሪዎች በተለያዩ የአለም አገራት በሚገኙ ከ100 በላይ ባንኮች ላይ በፈጸሙት ስርቆት በድምሩ 1 ቢሊዮን ዶላር መዝረፋቸውን ቢቢሲ ዘገበ፡፡ በኢንተርኔት ከተፈጸሙ መሰል የባንክ ዝርፊያዎች ከፍተኛው ገንዘብ የተሰረቀበት ነው የተባለው ይህ ዘረፋ፣ አጭበርባሪዎቹ በባንኮቹ ኮምፒውተሮች ላይ በጫኗቸው መረጃን የሚሰርቁ ሶፍትዌሮች አማካይነት የተከናወነ ሲሆን፣ በባንኮቹ ውስጥ የነበረው ገንዘብ አጭበርባሪዎቹ ወደከፈቱት የሃሰት አካውንት እንዲዘዋወር ተደርጓል፡፡
ካስፔርስኪ የተባለውን አለማቀፍ የኢንተርኔት ደህንነት ተቋም ጠቅሶ ዘገባው እንዳለው፣ አጭበርባሪዎቹ ከእያንዳንዱ ባንክ ከ2.5 ሚሊዮን እስከ 10 ሚሊዮን ዶላር ዘርፈዋል፡፡ እስከዛሬ ከተከናወኑት የባንክ ዘረፋዎች ሁሉ ፍጹም ውጤታማ እንደሆነ በተነገረለት በዚህ የኢንተርኔት ማጭበርበር ተግባር ሰለባ  የሆኑት ባንኮች ስም በይፋ ባይገለጽም፣ ባንኮቹ አሜሪካን ጨምሮ በተለያዩ 25 የአለማችን አገራት ውስጥ እንደሚገኙ ታውቋል፡፡
ዝርፊያው አሁንም እንደቀጠለ የጠቆመው ኩባንያው፣ ባንኮች የኮምፒውተር ሲስተሞቻቸው በዚህ የአጭበርባሪዎች ሶፍትዌር እንዳልተጠቁ ማረጋገጥና አስፈላጊውን ፍተሻና ጥንቃቄ ማድረግ ይገባቸዋል ብሏል፡፡

*200ሺ ሰዎች አመልክተው 100 ለመጨረሻው ዙር አልፈዋል
*4 ሴቶችና 1 ወንድ በማርስ የሪያሊቲ ሾው ፕሮግራም ይሳተፋሉ

ኤድሞል በተባለው ኩባንያ የሚዘጋጀውና አምስት ተፎካካሪዎችን የሚያካትተው የ2024  የቢግ ብራዘር የቴሌቪዥን ሪያሊቲ ሾው ፕሮግራም በማርስ ፕላኔት ላይ ሊዘጋጅ ነው፡፡
ኩባንያው በድረገጹ ላይ ባወጣው  መረጃ እንደጠቆመው ፣ ማርስ ዋን በተሰኘው ፕሮጀክት አማካይነት ከ9 አመታት በኋላ ወደ ማርስ  ሊደረግ የታቀደው ጉዞ አካል በሆነው የቢግ ብራዘር ላይ ለመሳተፍ 200 ሺህ ሰዎች ያመለከቱ ሲሆን  ለመጨረሻው ዙር ያለፉት 100 ሰዎች ተለይተዋል፡፡
ከ100ዎቹ እጩ ተፎካካሪዎች መካከል 39 አሜሪካውያን፣ 31 አውሮፓውያን፣ 16 እስያውያን፣ 7 አፍሪካውያን እና 7 አውስትራሊያውያን እንደሆኑ ታውቋል፡፡ በማርስ ላይ በሚከናወነው የ2024 የቢግ ብራዘር ሾው ላይ የሚሳተፉት አራት ሴት እና አንድ ወንድ ተፎካካሪዎች እንደሚሆኑ የተገለጸ ሲሆን  ጉዞው 3.6 ቢሊዮን ፓውንድ እንደሚፈጅ  ታውቋል፡፡ በማርስ ላይ የሚከናወነው ቢግ ብራዘር  በየሁለት አመቱ እንደሚዘጋጅ የጠቆመው መረጃው፣ ወደ ማርስ የሚደረገው ጉዞ 200 ቀናትን ያህል እንደሚፈጅም አስታውቋል፡፡

Saturday, 21 February 2015 13:58

“ሽርሽር” ገበያ ላይ ዋሉ

 በጀሚል አክበር የተፃፈው “ሽርሽር” የተሰኘ የአጭር ልብወለዶች ስብስብ ሰሞኑን ለንባብ በቅቷል፡፡ በመጽሃፉ ውስጥ 18 ያህል ታሪኮች የተካተቱ ሲሆን በ28 ብር ለገበያ ቀርቧል፡፡  ፀሀፊው ከዚህ ቀደም “ካገር ፍቅር እስከ አዲሳባ” የተሰኘ በእስረኞች ታሪክ ላይ የተመሰረተ መፅሀፍ ለንባብ ማብቃቱ የሚታወስ ሲሆን ታሪኩም በሸገር ሬዲዮ እንደተተረከ ደራሲው አውስቷል፡፡