Administrator

Administrator

የአፍሪካ 100 ምርጥ ዩኒቨርሲቲዎች ሰሞኑን ይፋ የተደረጉ ሲሆን የደቡብ አፍሪካዎቹ - ዩኒቨርሲቲ ኦፍ ሳውዝ አፍሪካ፣ ዩኒቨርሲቲ ኦፍ ኬፕታውንና ዩኒቨርሲቲ ኦፍ ስቴሌንቦስች ከአንደኛ እስከ ሦስተኛ ያለውን ደረጃ እንደወሰዱ “ፎር አይሲዩ” የተባለው ተቋም አስታወቀ፡፡
የታንዛኒያው ዩኒቨርሲቲ ኦፍ ዳሬሰላም በአራተኛነት ጣልቃ ቢገባባቸውም፣ ዩኒቨርሲቲ ኦፍ ኩዋዙሉ ናታል እና ዩኒቨርሲቲ ኦፍ ፕሪቶሪያ አምስተኛና ስድስተኛ ደረጃን  ይዘዋል፡፡ የግብጹ ካይሮ ዩኒቨርሲቲ ሰባተኛ፣ የደቡብ አፍሪካዎቹ ዩኒቨርሲቲ ኦፍ ዊትዋተርስራንድ እና ዩኒቨርሲቲ ኦፍ ዌስተርን ኬፕ ስምንተኛና ዘጠነኛ ደረጃን ሲይዙ የናይጀሪያው ኦባፌሚ አዎሎሎ ዩኒቨርሲቲ አስረኛ ሆኗል፡፡ የአገራችን አንጋፋው የአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ደግሞ  የ53ኛ ደረጃ እንደተሰጠው ለማወቅ ተችሏል፡፡
ግብጽ 20፣ ደቡብ አፍሪካ 19 ዩኒቨርሲቲዎችን በምርጥ መቶዎቹ ውስጥ በማስመረጥ፣ ቀዳሚነቱን የያዙ  ሲሆን  ኬኒያ 6፣ ሱዳን 2 ዩኒቨርስቲዎች ተመርጦላቸዋል፡፡
“ፎር አይሲዩ” የተባለው ተቋም በአህጉራት ደረጃ ምርጥ የሚላቸውን ዩኒቨርሲቲዎችና ኮሌጆች እየመረጠ በየስድስት ወሩ ይፋ ማድረግ የጀመረው እ.ኤ.አ ከ2004 ጀምሮ ነው፡፡ የዓለም ዩኒቨርስቲዎች የፈጠሩትን ተጽዕኖና በድረ ገጾች ላይ ያላቸውን የመረጃ ሽፋን መሰረት በማድረግ የምርጥ ዩኒቨርሲቲዎችን ዝርዝር ይፋ የሚያደርገው ተቋሙ፣ ተዓማኒ፣ ጠቃሚና መልከ ብዙ መረጃዎችን የመስጠት ዓላማ አለው፡፡ የትምህርትና የምርምር ተቋማት  የህትመት ስራዎችንና የምርምር ውጤቶችን በድረ ገጾች እንዲያሰራጩ የበለጠ ተነሳሽነት የመፍጠር ተጨማሪ አላማ እንዳለውም ለማወቅ ተችሏል፡፡

አንዳንድ ተረቶች በሂደት የዕውነታ ትንቢት ይሆናሉ፡፡ ቻይናዎች ዛሬ የደረሱበት ሁኔታ በሚከተለው ተረታቸው ላይ የተመሠረተ ሳይሆን አልቀረም፡፡
እነሆ፡-  
አንድ የቻይና ሊቅ-አዋቂ፣ አንድ ቀን በተከሰተለት ራዕይ ላይ ተመሥርቶ እንዲህ የሚል ሀሳብ ለህ/ሰቡ ያቀርባል፡-  
“ጐበዝ በመጪው ዘመን የሚመጣው ውሃ የተበከለ ነው የሚሆነው፡፡ ስለዚህ ካሁኑ በእጃችሁ ያለውን ንፁህ ውሃ ብታከማቹ ደግ ነው፡፡ መጪው ውሃ ከቶም ጥራት ያለው ስለማይሆን በጊዜ ውሃችሁን አጠራቅሙ፡፡”
ይህን በየቦታው እየዞረ መስበኩን ቀጠለ፡፡
ከፊሉ፤
“አጭበርባሪ ነው፡፡ አዋቂ ነኝ በማለት አዲስ ነገር ለማስመሰል የቆመ ነው፡፡”
ግማሹ፤
“ጊዜው እያለፈ ሲሄድ ፈላስፋ ነን የሚሉ መምጣታቸው አይቀሬ ነው፤ ተውት አትስሙት” የሚል እሳቤ አቀረበ፡፡
አዋቂው ግን፤
“ግዴላችሁም እኔ እምላችሁን ስሙ፡፡ ስለ ውሃ የወደፊት ሁናቴ የሚጠቅማችሁ ይሄ እኔ የምላችሁ ነገር ነው” ማለቱን ቀጠሉ፡፡
ሰው ሁሉ አዋቂውን ናቀ፡፡ ዘለፈ፡፡
ስለሆነም፤ አሮጌውን ውሃ ትቶ አዲስ ውሃ መጠጣት ፈቀደ፡፡ ጠጣ ጠጣና ሰው ሁሉ አበደ!
ከማ/ሰቡ መካከል አንድ ሰው ግን፤ አዋቂው ያለውን ተቀብሎ ውሃ ማጠራቀም ጀመረ፡፡ ሆኖም፤ የሰው ሁሉ መሳቂያ መሳለቂያ ሆነ፡፡ “ዕብድ ነው!” ተባለ፡፡ ይብስ ብሎ ተቃዋሚ አፈራ፡፡ ተቃዋሚው በዛ በዛና አገሩ ሁሉ ተቃዋሚው ሆነ፡፡ በዚህም ምክንያት ሰው ሁሉ፤
“ይሄ ሰው ጤና ቢጐለው ነው እንጂ የዱሮ ውሃ አያጠራቅምም ነበር፤ እያለ ክፉኛ ወሬውን ነዛው”
ሰውዬው፤ ከነጭራሹ በህብረተሰቡ ተተፋ፡፡ ንክ ነው፣ ዕብድ ነው ተባለ! የሚጠጋውም ሆነ የሚያወራው ወዳጅ በማጣቱ ይጨነቅ፣ ይጠበብ ጀመር፡፡ ያበደ አገር፤ እሱን ዕብድ ነው እያለ አገለለው!
ስለዚህ ዋለ አደረና ተስፋ ሲቆርጥ ያጠራቀመውን ውሃ ሁሉ ደፋው፡፡ ከዚያም እንደሰው አዲሱን ውሃ መጠጣት ጀመረ፡፡ ይሄኔ አገሬው፤ “ይሄ ዕብድ ጤናው ተመለሰ፡፡ ደህና ሰው ሆነ!” እያለ እያወደሰው፣ ቀርቦ ያጫውተው ጀመር፡፡ ያ ዕብድ የተባለ ሰው ከአገር ተደባለቀ፡፡ ከዕድር ተዋሃደ፡፡ ካበደው አበደ፡፡ ነባሩን ጽዱ ውሃ ያጠራቀመ ሰው በአገሩ ባለመኖሩ፤ ሰው ሁሉ የተመረዘው፣ አዲስ ውሃ ሰለባ ሆነ!!
*    *    *
ከመንገደኝነት አስተሳሰብ ካልወጣን ንፁህ ውሃ አንጠጣም፡፡ በአንድ አሸንዳ የመፍሰስ አባዜ ለለውጥ አያዘጋጅም፡፡ የተለየ አስተሳሰብ ያላቸውን ወገኖች እህ ብለን ካላዳመጥን ለውጥ አናመጣም። ምክንያቱም፤ አንቻቻልምና ሰላም አይኖረንም፡፡ አንተራረምምና ከስህተት ክብ ቀለበት ለመውጣት አይቻለንም፡፡
ሀገራችን፤ ሁለመናቸው ዓይን ብቻ የሆኑ (እለ ኩለንታሆሙ መሉዐነ ዓእይንት እንዲል ግዕዙ) ሰዎች የሚያስፈልጓት ሰዓት ላይ ናት፡፡ ደራሲ ብርሃኑ ድንቄ በ “አልቦ ዘመድ” እንደገለፁት፤ “የኢትዮጵያን ታሪካዊ ባህል አስፋፍቶ ለማሳደግና መሠረቱንም ለማጠንከር የደከሙት፤ “እብነ ማዕዘንት” የሚባሉት አባቶች ሁሉ አልቀው፤ ዛሬ ኮረቶቹና ጠጠሮቹ መሠረት ነን እያሉ ሲፎክሩ መስማት ‘ትራጀዲ’ ብቻ አይባልም፡፡ ‘ኮሜዲም’ መሆን አለበት፡፡ ይህን ዝብርቅርቅ ሳስብ በማልቀስ ፈንታ አንዳንድ ጊዜ ያስቀኛል፡፡ ‘እንዳላለቅስ ብዬ በመፍራት ሁልጊዜ እስቃለሁ’ ብሎ የተናገረው ማነው?” ይሉናል። ጥቅሱ የፀሐፌ-ተውኔቱ የቦማርሼ ነው፡፡ አፍንጫችን ሥር ያለውንና የፊት የፊታችንን ብቻ ስንመለከት መሠረታችንን እንዳንስት በቅጡ ማስተዋል ይገባናል፡፡ መሠረቱ የላላ ህብረተሰብ የኋላ ኋላ፤ ራሱንም አጥቶ የሌላውንም መቀበል ሳይችል አየር ላይ ተንገዋሎ ይቀራል፡፡ ለጊዜው የሥልጣኔ የሚመስሉን፣ ከነስውር - ደባቸው ማንነታችንን ሊያጨነግፉ የሚባትቱ አያሌ መጤ የካፒታሊዝም ሳልባጅ አስተሳሰቦችን በጥንቃቄ ማየት አለብን፡፡ እነዚህን ትውልድ ሳንገነባ ልንታገላቸው አንችልም። የሚከተለው ቃል ትውልዳችንን ለማየት ይጠቅማልና እነሆ፡- “ያለፈውን ትውልድ የሚያደንቁበት፣ የዛሬውን ትውልድ የሚፈርዱበት ዋናው ምክንያት ምንድን ነው? …” ተብለው አንደኛው ገፀ - ባህሪ ይጠየቃሉ፡፡ ሌላው ሲመልስ -  
“በነዚህ ሁለት ቃላቶች ላይ የእኔን ምክንያቶች ተንጠልጥለው ያገኙዋቸዋል፡-
፩ መስዋዕትነት ፪ ራስን መውደድ፡፡ ያለፈው ትውልድ መስዋዕትነት ምን እንደሆነ ደህና አድርጎ ያውቃል፡፡ የዛሬው ትውልድ ደህና አድርጎ የተማረው ራስን መውደድ ነው!!” (አልቦ ዘመድ)
አንድ ትውልድ መስዋዕትን ሳያቅ ጥቅም እንደሚያገኝ ሲያስብ ሐሳቡ እንደጧት ጤዛ እየተነነ፣ የጨበጠው የመሰለውና ያዝኩት የሚለው ነገር ሁሉ እየበነነ፣ መንፈሰ - ባዶነት ስለሚያጠቃው፣ መቦዘን፣ መንገዋለልና የማናቸውም አዲስ ሀሳብ፣ አዲስ ግጭት ሰለባ የመሆን ዕድሉ ሰፊ ነው፡፡ ስለሆነም በብሔር-ብሔረሰቡም፣ በሃይማኖቱም፣ በፍልስፍናውም፣ በማህበራዊ ቀውሱም፣ እንዲያው ባገኘው ክስተት ውስጥ ሁሉ ጠብ-ያለሽ-በዳቦ ማለትን፣ ተንኳሽነትን፤ ሽፋጭነትን፣ ዘራፊነትን ያስተናግዳል። ሰከን፣ ጠንፈፍ ብሎ ስለማይቀመጥ ትግሉ ሁሉ ብትን ይሆናል፡፡ የመደራጀት፣ የመሰባሰብ የመወያየት፤ መላ ይጠፋበታል! ጊዜ ወስዶ የመብሰል ነገር ይሳነዋል፡፡ ኑሮ ያራውጠዋልና መንፈሱ እየባዘነ ያገኘውን ሁሉ ቀጨም የማድረግ ፈሊጥን ብቻ ያዘወትራል፡፡ የበለጠ ከሥሩ ይነቀላል። ንቀትን እንደዕውቀት ምንጭ ስለሚይዝ፤ ሁሉን ነገር በቅድመ-ፍርድ (bias) ወስኖ፤ አዕምሮውን ዘግቶ፣ ፋይሉን ወደ መዝገብ ቤት መልሶ፣ ስለሚቀመጥ የመለወጥ ዝግጁነት ከቶ ያጣል፡፡ ስለሆነም ከጥቅም ማጋበስ ውጪ የሚታየው ነገር አይኖርም፡፡ በአፉ ይራገማል፣ ድርጊቱን ግን ራሱ ሲፈፅመው ይታያል፡፡ የህ/ሰብ ዝቅጠት (degeneration) ምልክት ነው፡፡ የንቅዘት (decadence) መገለጫው ነው፡፡ ከዚህ ሁሉ ባሻገር ደግሞ የአንጎላችን ባዶነት ሳያንስ፣ በድህነታችን ጥልቀት ሳቢያ ሆዳችን ባዶ ሆኖ ሲጮህብን፣ ጉሮሮአችን ደርቆ ሲሰነጣጠቅብን ዓመት በዓል ሲመጣብን፣ ሌማታችን ባዶ ሲሆን፣ ህይወት የምሬት ሬት ወደመሆን ያመራና፤ ዕቅዱ፣ ራዕዩ፣ ስትራቴጂው፣ ታክቲኩ፣ ፖለቲኩ፣ ምርምሩ ሁሉ፤ ይቀርና ከልቡናችንም ይፋቅና፣ ይጠፋና፤ “ነገ ነዳጅ ሊወጣ ነው”፣ “ተቆፍሮ ወርቅ ሊፈልቅ ነው” ቢባል፣ “ከሚመጣው ዓመት ዶሮ፣ ዕንቁላል ዘንድሮ!” ማለት ብቻ ይሆናል ቋንቋችን! ለማንኛውም መልካም የገና (“ገ” ጠብቆም ላልቶም) በዓል ይሁንልን!!
እንኳን ለልደት በዓል አደረሳችሁ!

          የአፍሪካ ነባር ባህል፣ ባለፉት 25 አመታት ምን ያህል እንደተረዘ በግልፅ አየነው - በደቡብ ሱዳን። ተቀናቃኞቹ ወገኖች፣ ገና ተኩስ ከመጀመራቸው፣ በጦርነት የመቀጠል ፋታ አልተሰጣቸውም። በቃ፣ በድንበር መዋጋት ወይም እርስበርስ እንደልብ መፋጀት ከእንግዲህ ለአፍሪካዊያን አይፈቀድም ማለት ነው?
ድሮኮ እንዲህ አልነበረም። ግጭትን ከትውልድ ትውልድ ማውረስና ማሸጋገር የለመደ አህጉር፣ አሁን ጦርነት ተከልክሎ ምን ሊውጠው ነው? ቢያንስ ቢያንስ፣ አስር አመት ወይም ሃያ አመት መዋጋት ለአፍሪካ ብርቅ አልነበረም፡፡ ኢትዮጵያ፣ አንጎላ፣ ሞዛምቢክ፣ ደቡብ አፍሪካ... እና ሌሎች ከደርዘን የሚበልጡ የአፍሪካ አገራትን መጥቀስ ይቻላል። አይገርምም? ዛሬ ከሶማሊያና ከኮንጎ በስተቀር፣ የያኔዎቹ የጦርነት አውድማዎች ከሞላ ጎደል ሰላም አግኝተዋል። የብዙዎቹ አገራት የእርስ በርስ ጦርነት እየከሰመ ጠፍቷል ወይም ረግቧል። በአንዱ ወይም በሌላው አገር አዲስ ግጭት ስንለኩስም፣ በጦርነት በርካታ ወራትና አመታት ሳይቆጠሩ ፍጅቱን በአጭሩ ለመቅጨት መሯሯጥ ተለምዷል።
አሁን አሁንማ፣ ፈፅሞ ለጦርነት ጊዜ የሚሰጠን ሰው እየጠፋ ነው። ደቡብ ሱዳንን ተመልከቱ። ለአዲስ ጦርነት የተነሳሱት ባላንጣዎች፤ የአንድ ሳምንት የውጊያ ጊዜ እንኳ አላገኙም። ከግራና ከቀኝ፣ ከጎረቤትና ከሩቅ፣ ከጓዳና ከአደባባይ... አለም ሁሉ “ተረጋጉ፣ እረፉ፣ አደብ ግዙ” እያለ ዘመተባቸው። “ጦርነት ካልቆመ እመጣላችኋለሁ” የሚል ማስፈራሪያ ከሰነዘረችው ከኡጋንዳ ጀምሮ እስከ አሜሪካ፣ ከአፍሪካ ህብረት እስከ ዩኤን፣ ከኢትዮጵያ እስከ ቻይና፣ ከኢጋድ እስከ አውሮፓ፣ በግልና በቡድን ድምፁን ያላሰማ የለም ማለት ይቻላል። እንደየዝንባሌው፣ ገሚሱ ሸምጋይና አደራዳሪ፣ አንዳንዱ ተቆጪና መካሪ፣ ሌላኛው ገላጋይና ሰላም አስከባሪ እየሆነ፣  አለማቀፉ ማህበረሰብ (አዳሜ በሙሉ) ከየአቅጣጫው ሲያጣድፋቸው፣ ደቡብ ሱዳኖች ሳይደነግጡ አይቀሩም።
በቃ፣ “እንደልብ መዋጋትና እድሜ ልክ መፋጀት ድሮ ቀረ!” ልንል ነው? ድሮ ድሮኮ፣ አፍሪካዊያን እንዳሻቸው በጦርነት ቢፋጁ ከልካይ አልነበራቸውም። ደግሞም አይገርምም። በብዙ የአፍሪካ አገራት፣ የአንዱ ጎሳ ተወላጆች፣ በሌላ ጎሳ ተወላጆች ላይ እየዘመቱ፣ ከብት መዝረፍና መንደር ማቃጠል፣ አካል መቁረጥና በጅምላ መግደል፣ ከጥንት ጀምሮ የተለመደ ነባር ባህል ነው። ስሙን እናሳምረው ካልን፣ “ቱባ ባህል” ልንለው እንችላለን - ለረዥም ዘመን ዛይበረዝና ሳይከለስ የዘለቀ! ጥንታዊው የጎሳ ዘመቻ፣ በሃያኛው ክፍለዘመንም ቢሆን፣ ከዘመኑ አኗኗር ጋር መልኩ ቢቀየርም ጨርሶ አልቀነሰም። እንዲያውም ይበልጥ ሲጧጧፍና ዘግናኝነቱ ሲብስበት ነው ያየነው። በቋንቋና በብሄረሰብ ወይም በፖለቲካ ድርጅት ተቧድኖ መጨፋጨፍ፣ የአፍሪካ መለያ ባህርይ እስከመሆን የደረሰው በ20ኛው ክፍለዘመን አይደል?
ኢትዮጵያ ውስጥ በእርስበርስ ጦርነት ከ150 ሺ ሰው በላይ፣ በኢትዮኤርትራ የድንበር ጦርነትም ከ70 ሺ ሰው በላይ አልቋል። በላይቤሪያ የሰባት አመታት ጦርነትም እንዲሁ 150 ሺ ሰው ሞቷል። የአፍሪካውያን የጦርነት ሱስና የፍጅት ባህል ባይቀየርም፤ ፍጅቱ እየበዛ የመጣው አለምክንያት አይደለም። ዛሬ በዘመናችን፣ እንደጥንቱ በጎራዴና በጦር ሳይሆን፣ በክላሺንኮቭና በታንክ ነው የሚጨፋጨፉት። አንጎላዊያን ለሃያ አመታት ባካሄዱት የእርስ በርስ ጦርነት፣ የግማሽ ሚሊዮን ሰዎች ህይወት ጠፍቷል። በሱዳን የዳርፉር ግዛት፣ በሁለት አመታት ግጭት ሰበብ ሁለት መቶ ሺ ሰዎች ሞተዋል። በሴራሊዮንም እንዲሁ፣ ከሞተው ህዝብ የማይተናነስ ቁጥር ያላቸው ሰዎች፣ በጭካኔ እጃቸው ተቆርጧል።
ታዲያ፣ ያ ሁሉ ሰው ያለቀው፣ “ሕዝቡን ከቅኝ ግዛት ነፃ አውጥተናል” በሚሉ ሶሻሊስት መሪ፣ ወይም “ሕዝቡን ከአምባገነን መሪዎች ነፃ እናወጣለን” በሚሉ ሶሻሊስት አማፂዎችና አገር ወዳድ አርበኞች አማካኝነት ነው። እርስ በርስ ሲጨፋጨፉ፣ “አለማቀፉ ማህበረሰብ” ምን ይሰራ ነበር ትሉ ይሆናል። አንዳንዱ፣ በእሳት ላይ ቤንዚን በማርከፍከፍ ጦርነቱን ያባብሳል። አንዳንዱ፣ “እንደፍጥርጥራቸው” ብሎ አይቶ እንዳላየ ኑሮውን ይቀጥላል። ነገር ግን፣ ተግሳፅና ምክር ለመለገስ የተጣጣሩ አልነበሩም ማለት አይደለም። ገላጋይና አስታራቂ ለመሆን የሞከሩ አልጠፉም። ቢሆንም ሰሚ አላገኙም። እንዲያውም ስድብ ነው የተረፋቸው። “በውስጥ ጉዳያችን ላይ ጣልቃ አትግቡብን፤ የእጅ አዙር ቅኝ ገዢዎች ናችሁ” ተብለው ይዘለፋሉ። የአፍሪካ አንድነት ድርጅት፣ ዋነኛ መርህ “በአገራት የውስጥ ጉዳይ ላይ ጣልቃ አለመግባት” የሚል እንደነበረ አታስታውሱም? አፍሪካዊያን “ጣልቃ አትግቡብን” እያሉ የሚከራከሩት፤ እያንዳንዱ አገር የውስጥ ጉዳዩን በራሱ ምርጫ እየመራ ተከባብሮ ለመኖር በማሰብ እንዳይመስላችሁ። ያለከልካይ እርስ በርስ ለመተላለቅ ነው።
የአፍሪካዊያን እልቂት ከጣሪያ በላይ አልፎ አለምን ለማስደንገጥ የበቃው ግን፣ በሩዋንዳ ከዚያም በኮንጎ በተከሰቱ ዘግናኝ ጦርነቶችና ግጭቶች ነው። በአንድ አመት የእርስ በርስ ፍጅት ነው፣ ከአንድ ሚሊዮን በላይ ሩዋንዳዊያን የረገፉት። የኮንጎ ደግሞ የባሰ ነው። ጦርነትና ረሃብ ተደማምሮ፣ በአስር አመታት ውስጥ፣ 5.4 ሚሊዮን የኮንጎ ሰዎች መሞታቸውን አለማቀፉ የቀይመስቀል ድርጅት ገልጿል።
ደግነቱ፣ ከቅርብ አመታት ወዲህ፣ አፍሪካዊያን ጥንታዊ የጦርነት ሱሳቸውንና የፍጅት ባህላቸውን የሙጢኝ ይዘው መቀጠል አልቻሉም። ምክንያቱ ሚስጥር አይደለም፡፡ የጥንቱ የፍጅት ባህል እና ዘመናዊ የጦር መሳሪያ ሲቀላቀሉ ነው፤ አህጉሪቱ በደም የታጠበችው። በጥንቱ ዘመን፣ አፍሪካዊያን ብዙ ሰውዎችን የመግደል ፍላጎት እንጂ ብዙ ሰዎችን የመግደል አቅም አልነበራቸው። ሹል እንጨት ቀስሮ ለጦርነት የሚዘምት ተዋጊ፣ አገር ምድሩን የመጨፍጨፍ እድል አያገኝም። እንጨቱ ይዶለዱማል ወይም ይሰበራል። አልያም እያሳደደ ሲገድል ውሎ፣ አመሻሹ ላይ ደክሞት ይዝለፈለፋል። ባደክመው እንኳ ጊዜ አይበቃውም - እያንዳንዱን ሰው ማሳደድና በእንጨት መውጋት ከባድ ፈተና ነው። ክላሺንኮቭ ታጥቆ በእሩምታ ደርዘኖችን መረፍረፍ፣ በታንክ መንደሮችን ማረስ የቻለ ጊዜ ነው፤ ጥንታዊ የፍጅት ባህል ምን ያህል ዘግናኝ እንደሆነ ጎልቶ መታየት የጀመረው። ጥንታዊ ባህልን ይዞ ዘመናዊ የጦር መሳሪያ የታጠቀው የአፍሪካ ሕዝብ፣ ብዙም በሕይወት የመቆየት እድል እንደሌለው በአህጉሪቱ ከተከሰቱ እልቂቶች መረዳት ይቻላል።
እናስ ምን ተሻለ? ያለከልካይ የመጨፋጨፍ ቱባ ባህል የግድ ተወግዶ፣ በምትኩ ተከባብሮ የመኖር ባህል መፈጠር አለበት። በዚህ ምክንያት፣ “ወግና ልማድ ተሻረ፤ ቱባ ባህል ተበረዘ” የሚል ቁጭት የሚያድርባቸው ሰዎች ይኖሩ ይሆን? የሚኖሩ ከሆነ፤ “ነገር የተበላሸው በ1980ዎቹ መጀመሪያ ነው” ማለታቸው አይቀርም። እውነትም፤ ኢትዮጵያንና ጎረቤቶቻችንን ጨምሮ፣ በአህጉሪቱ አራት አቅጣጫዎች፣ የጥንቱን ባህል የሚቃረን የለውጥ አየር ከዳር እስከ ዳር የነፈሰው፣ ያኔ ነው። የለውጡ መጠንና የነፋሱ ጉልበት፣ እንደየአገሩ ሁኔታ ይለያያል። የአንዳንዶቹ ፈጣን ሲሆን፣ የሌሎቹ ዘገምተኛ ነው። ገሚሶቹ፣ በእመርታ ሲራመዱ፤ ገሚሶቹ ይንፏቀቃሉ። ከፊሎቹ ያለማቋረጥ ሲሻሻሉ፤ ከፊሎቹ መነሳትና መውደቅ ያበዛሉ። ጠንካራ መሠረት የተከሉ እንዳሉ ሁሉ፣ ከአፍታ እልልታ በኋላ ወደ ዋይታ የተመለሱም አሉ። ከጦርነት ለመላቀቅ ጊዜያዊ መፍትሄ ማበጀትና የተኩስ አቁም ስምምነት መፈረም ብቻውን በቂ አይደለማ፤ ተከባብሮ ለመኖር ዘላቂ መላ መፍጠር ያስፈልጋል።
የሆነ ሆኖ፣ መጠኑና ደረጃው ቢለያይም፤ በ80ዎቹ ዓ.ም መግቢያ ግድም፣ በአዲስ የለውጥ ነፋስ ያልተነካ የአፍሪካ አገር የለም ማለት ይቻላል። በአፍሪካ የለውጥ አየር የነፈሰው፤ በራሺያ መሪነት አለምን ሲያተራምስ የነበረው የሶሻሊዝም ስርዓት በተፈረካከሰ ማግስት መሆኑ አይገርምም። ያው እንደምታውቁት፣ በሶሻሊዝም ስርዓት ተከባብሮ መኖር አይቻልም።
ሶሻሊዝም ማለት የአንድ ፓርቲ፣ የአንድ ቡድን ወይም የአንድ ግለሰብ አምባገነንነት ስለሆነ፤ የፈላጭ ቆራጭነትን ስልጣን ለመያዝ፣ የግድ መጠፋፋትና መፋጀት ያስፈልጋል። ብዙዎቹ የአፍሪካ መንግስታትና አማፂ ሃይሎች፣ ሶሻሊስት ለመሆን የተሯሯጡት ለምን ሆነና! ሶሻሊዝም ከጥንታዊው አፍሪካዊ የፍጅትና የጦርነት ባህል ጋር ይጣጣማላ። ደግነቱ፣ በ1980 ዓ.ም መፍረክረክ የጀመረው የሶሻሊዝም ስርዓት፣ በ1983 ዓ.ም ሶቭየት ዩኔን ስትበታተን ነው ተፈረካክሶ አበቃለት። ይሄው የለውጥ ነፋስ፣ አፍሪካን ለማዳረስ ጊዜ አልፈጀበትም። እንዴት በሉ።
ከዚያን ጊዜ በፊት፣ በአፍሪካ ለስም ያህል፣ የፓርቲዎች ፉክክርና የምርጫ ውድድር የሚያካሂዱ አገራት ከሁለትና ከሶስት አይበልጡም ነበር። አንዷ ቦትስዋና ናት። በተወሰነ ደረጃ ደግሞ፣ ሴኔጋል ትጠቀሳለች።
ሌሎቹ አገራት በሙሉ ማለት ይቻላል፤ የአንድ ፓርቲ አገዛዝ የነገሰባቸውና፣ “ተቃዋሚ ፓርቲ ማቋቋም በእስር ወይም በሞት የሚያስቀጣ ወንጀል ነው” የሚል ህግ ያወጁ፤ ከዚህም ጋር ተያይዞ፣ ለበርካታ አመታት በእርስ በርስ ጦርነት የሚታመሱ አገራት ነበሩ። አማፂው ሃይል፣ በጦርነት አሸንፎ ስልጣን ሲቆናጠጥም፣ በተራው የአንድ ፓርቲ አምባገነንነትን ስለሚያሰፍን ሌላ ዙር ጦርነት ይቀጣጠላል። ማብቂያ በሌለው የአምባገነንነትና የፍጅት አዙሪት ውስጥ በነበረችው አህጉር ላይ፣ አዲስ የለውጥ አየር ሲነፍስ ይታያችሁ። በጦርነት ብዛትና በአንድ ፓርቲ አገዛዝ የተጥለቀለቀችው አህጉር፣ በሰላም ድርድርና በአዳዲስ የህገመንግስት ረቂቆች ተጥለቀለቀች።
ለምሳሌ ለረዥም አመታት በአንጎላ፣ በሞዛምቢክና በኢትዮጵያ ሲካሄዱ የነበሩ ጦርነቶች እልባት ያገኙት በተመሳሳይ ጊዜ ነው። እነዚህ ሶስት የጦርነት አገራትን ጨምሮ፣ ኬንያና ደቡብ አፍሪካ፣ ጋና እና ናይጄሪያ፣ ኒጀር እና ዛምቢያ፣ ታንዛኒያና ኬኒያን…ምን አለፋችሁ? ከሰሃራ በታች፣ 25 ገደማ አገራት፣ የፖለቲካ ፓርቲዎችን ለማቋቋም የሚፈቅድ ህገመንግስት ያዘጋጁትና ፓርቲዎች የሚፎካከሩበት ምርጫ ማካሄድ የጀመሩት ከ1982 እስከ 1987 ዓ.ም ባሉት አምስት አመታት ነው። በቃ፤ ከዚያን ጊዜ ወዲህ ነው፣ የነፃነት ሜዳው ሰፊም ሆነ ጠባብ፣ የፖለቲካ ምርጫ የማያካሂድ አገር እንደ ነውረኛ መታየት የጀመረው። አሁን እንደ ኤርትራና ሱዋዚላድ ከአለም የተገለሉ አገራት ካልሆኑ በቀር፤ የአንድ ፓርቲና የአንድ ግለሰው አምባገነንነትን በአዋጅ የሚያሰፍን የአፍሪካ አገር የለም ማለት ይቻላል። ከዚሁ ጎንም ነው፤ “ያለከልካይ እንደልብ በእርስበርስ ጦርነት የመፋጀት ባህል” የተበረዘው።
የምታስታውሱ ከሆነ፣ ኢትዮጵያ ውስጥ ለሃያ አመታት ያህል፣ የእርስ በርስ ጦርነት ሲካሄድ፣ አለም “እሪ” አላለብንም። ሊያስቆመን አስቦ እጁን ያስገባ ማንም የለም። የሰላም አስከባሪ ሃይል ማሰማራትማ ጨርሶ አይታሰብም ነበር። ያለገላጋይ እስኪለይለት ድረስ መፋጀት ነው። ከ1980ዎቹ ዓ.ም ወዲህ፣ በተለይ ከርዋንዳው እልቂት በኋላ ግን፣ አዲስ ጦርነት በተቀሰቀሰ ቁጥር፣ አለም እሪ ይላል። ሳምንት ሳይሞላው፣ ጎረቤት አገራት አደራዳሪ ቡድን ያቋቁማሉ። የአፍሪካ ህብረት የአቋም መግለጫና ውሳኔ ያስተላልፋል። ዩኤን በበኩሉ፣ በኬንያና በሱዳን፣ በላይቤሪያና በርዋንዳ እንደታየው፣ የጅምላ ጭፍጨፋ ያካሄዱ መሪዎች ላይ ምርመራ ለማካሄድና ወደ አለማቀፉ የወንጀል ፍ/ቤት ለመውሰድ ይዝታል፡፡ አሜሪካና አውሮፓ በፊናቸው የዲፕሎማሲ ዘመቻ ይከፍታሉ።
በዚህ መሃል፣ “አልደራደርም፤ እንዳሻኝ እዋጋለሁ፤ በውስጥ ጉዳይ ጣልቃ አትግቡብኝ” ለማለት የሚደፍር ማን ነው? ዋጋውን ያገኛታላ። ጎረቤት አገራት ጦር ይልካሉ። የምዕራብ አፍሪካ አገራት ወታደሮቻቸውን ወደ ላይቤሪያ አዝምተው አልነበር? ኢትዮጵያና ኬንያም፣ ጦራቸውን ወደ ሶማሊያ አስገብተዋል። አሜሪካና አውሮፓም፣ እንደሁኔታው፣ ሊቢያ ላይ እንዳደረጉት የጦር አውሮፕላን ይልካሉ። ወይም እንደ ፈረንሳይ እግረኛና ኮማንዶ ጦር ያዘምታሉ። የተባበሩት መንግስታት እንኳ፣ እንደድሮው፣ ሰላምን የሚጠብቅ (Peace Keeping) ታዛቢ ሃይልን አይደለም የሚያሰማራው። በእርግጥ ስሙ አልተለወጠም። ተግባሩ ሲታይ ግን፤ “ሰላም አስከባሪ ተዋጊ ሃይል” ብለን ልንጠራው እንችላለን። በኮንጎ፣ በሴራሊዮንና በላይቤሪያ እንዳየነው፤ የተባበሩት መንግስታት ጦር፣ ለእርቅ እምቢተኛ ሆነዋል የተባሉ አማፂ ቡድኖችን እያሳደደ ወግቷል። አንዳንዳችን አስሮ ለፍርድ አቅርቧል፡፡ በተባበሩት መንግስታት ድጋፍ ወደ ሶማሊያ የዘመተው የአፍሪካ ህብረት ጦርም፣ ከአልሸባብ ጋር ይዋጋል።
በአጭሩ፣ ጊዜው ተለውጧል። እንደ ድሮ አይደለም፣ ዛሬ “አለከልካይ መፋጀት ለአፍሪካዊያን አይፈቀድም” የሚል ስሜት በርክቷል። ይሄውና የደቡብ ሱዳን ተቀናቃኝ ወገኖች፤ ገና ወደ ጦርነት በገቡ ሳምንት፣ በሰላም ጥሪ መውጪያ መግቢያ አጥተዋል።

በዕውቋ ድምፃዊት ዘሪቱ ከበደ ተፅፎ የተዘጋጀው “ቀሚስ የለበስኩለት” የተሰኘ ፊልም በሚቀጥለው ሳምንት እሁድ በአፍሪካ ህብረት አዳራሽና በአዲስ አበባ ሲኒማ ቤቶች  ይመረቃል፡፡ የድራማ ዘውግ ባለው  የ1፡40 ደቂቃ ፊልም ላይ፤ ድምፃዊቷ ዘሪቱ ከበደ፣ የንግድ ም/ቤት ፕሬዚዳንቷ ሙሉ ሰለሞን፣ የጃኖ ባንዱ ድምፃዊ ዲበኩሉ ታፈሰ፣ ሙዚቀኛው ሄኖክ መሐሪ፣ ይስሃቅ ዘለቀና ሌሎችም እንደተወኑበት ታውቋል፡፡ ፊልሙን ሰርቶ ለማጠናቀቅ ሁለት ዓመት የፈጀ ሲሆን ቀረፃውን “የሳቢሳ ፊልሞች” እንዳከናወነው ለማወቅ ተችሏል፡፡

የአፍሪካ ሞዛይክ የፋሽንና የባህል ትርኢት በሚቀጥለው አርብ ምሽት በሸራተን አዲስ የሚካሄድ ሲሆን በዝግጅቱ አለማቀፍ የፋሽን ሞዴሎችና ዲዛይነሮች ይሳተፋሉ፡፡ የአፍሪካን ሞዛይክ ዳይሬክተር አና ጌታነህ እንደገለፀችው፤ አስራ አምስት የውጪና የሀገር ውስጥ ዲዛይነሮች በሚሳተፉበት ትርኢት፤ እውቅ የዘርፉ  ባለሞያዎች ከኒውዮርክ፣ ከደቡብ አፍሪካና ከሴኔጋል ይመጣሉ፡፡ የኢትዮጵያ ምርጥ ሃያ ሞዴሎች የሚሳተፉበት የፋሽን ትርኢት ምሽት የመግቢያ ዋጋ 500 ብር ሲሆን ገቢው ከአዲስ አበባ 55 ኪ.ሜ ርቀት ላይ በምትገኘው አለልቱ ከተማ ለሚካሄደው የተቀናጀ ልማት ፕሮጀክት ይውላል ተብሏል፡፡ የአፍሪካ ሞዛይክ የፋሽንና የባህል ትርኢት በአዲስ አበባ ሲካሄድ የአሁኑ ለአስራ አራተኛ ጊዜ መሆኑ ታውቋል፡፡

በእናቱ ኢትዮጵያዊ፣ በአባቱ ሆላንዳዊ በሆነው ዳንኤል ጁፕሁክ የተፃፈውና በእውነተኛ ታሪክ ላይ የሚያጠነጥነው “አመፀኛው ክልስ” የተሰኘ መጽሐፍ ሰሞኑን በገበያ ላይ ዋለ፡፡ ደራሲው በ12 ዓመት የእስር ቤት ቆይታው ያሳለፈውን ህይወት ከወህኒ ቤት ከወጣ በኋላ በደች ቋንቋ እንደፃፈው፣ ከዚያም ወደ አማርኛ በመተርጎም እንዳሳተመው ታውቋል፡፡
በአማርኛ ቋንቋ የተተረጐመው መጽሐፍ፤ በአገር ውስጥ በ70 ብር እየተሸጠ ሲሆን በደች ቋንቋ የተዘጋጀው ደግሞ በደቡብ አፍሪካና በአውሮፓ በመሸጥ ላይ እንደሆነ ያገኘነው መረጃ ይጠቁማል፡፡

በአሚር ዩኒስ ረሐስ የተፃፈው “የምሥራቅ ፈርጦች” የተሰኘ ታላላቅ የሐረሪ ተወላጆችን ታሪክ የያዘ መፅሃፍ ባለፈው ሳምንት ለንባብ በቅቷል፡፡ ስምንት የሚደርሱ የሐረሪ ሊቃውንቶችና የታሪክ ምሁራንን የሚያስተዋውቀው መፅሃፉ፤ መታሰቢያነቱን የሥነ ጽሑፍ ባለሙያ ለነበሩት ለአብዱል ሐፊዝ ከሊፋ መሐመድ እና ለመሐመድ ኢብራሒም ሱሌይማን አድርጓል፡፡
በመጽሐፉ ታሪካቸው ከተካተቱት መካከል የሳይንስ ሊቁ ፕሮፌሰር ዘኪ አብዱላሒ፣ የታሪክ ምሁሩ አህመድ ዘካሪያ፣ የሐረር የነፃነት አባት በሚል የተገለፁት ሼህ ኢብራሂም ጋቱርና ሌሎች ለሐረሪ ህዝብና ለኢትዮጵያ እድገት አስተዋጽኦ ያበረከቱ ግለሰቦች ይገኙበታል፡፡ ግለሰቦችም ትውልድ ሊማርበት የሚችል  አኩሪ ታሪክ አላቸው የሚለው ደራሲው፤ በመፅሃፉ ታላላቅ ሥራዎችን የሰሩና የታሪክ ባለውለታ የሆኑ የጥቂት ሐረሪዎችን ታሪክ ለመዳሰስ መሞከሩን በመግቢያው ላይ ገልጿል፡፡ በ413 ገፆች የተቀነበበው መፅሃፉ፤ በ80 ብር ለገበያ ቀርቧል፡፡
በሌላ በኩል በገጣሚ አለማየሁ ነጋ የተፃፉ ግጥሞችን ያካተተ ‹‹የተመዘዙ ሰበዞች›› የተሰኘ የግጥም መድበል ታትሞ ባለፈው ሳምንት  ለገበያ ቀርቧል፡፡ በ72 ገፆች ሰባ ሁለት ግጥሞችን የያዘው የግጥም መፅሐፍ በ30 ብር እየተሸጠ ነው፡፡

የፌዴሬሽን ምክር ቤት በፓርላማ የወጣውን ህግ ሲያሻሽል አሁን የመጀመሪይው ነው፡፡ የቀድሞ መከላከያ ሚኒስትር አቶ ስዬ አብርሃ ተመሳሳይ ጥያቄ አቅርበው ውድቅ ተደርጐባቸው ነበር፡፡
“በሚኒስትር ማዕረግ የገቢዎችና ጉምሩክ ባስልጣን ዋና ዳሬክተር አቶ መላኩ ፈንታ ላይ የቀረበው የሙስና ክስ መታየት ያለበት በከፍተኛ ፍ/ቤት ነው ወይስ በጠቅላይ ፍ/ቤትን” በሚል ለተነሳው ጉዳይ ምላሽ ለመስጠት ለሰዓታት የተከራከሩ የፌደሬሽን ምክር ቤት አባላት፤ የሚኒስትሮች ክስ በጠቅላይ ፍ/ቤት እንዲታይ የሚደነግገው አንቀጽ ከፀረ ሙስና አዋጁ እንዲሰረዝ በ76 የድጋፍና በ8 የተቃውሞ ድምጽ ወሰኑ፡፡
የሙስና ክሶችን በቀዳሚነት የመዳኘት ስልጣን የከፍተኛ ፍ/ቤት እንደሆነ የሚገልፀው የፀረሙስና አዋጅ፣ ሚኒስትሮች ሊከሰሱ ግን በቀጥታ ወደ ጠቅላይ ፍ/ቤት እንደሚቀርብ ይገልፃል፡፡ በ1993 ዓ.ም ኢህአዴግ ውስጥ በተከሰተው ፀብ ከፓርቲው አመራርነት የተባረሩት የቀድሞ መከላከያ ሚኒስትር ስዬ አብርሃ፣ በወቅቱ በሙስና መከሰሳቸው የሚታወቅ ሊሆን፣  ጉዳያቸው በቀጥታ በጠቅላይ ፍ/ቤት እንዲታይ መደረጉን ተቃውመው እንደነበር ይታወሳል፡፡ እንደሌሎች ተከሳሾች የአቶ ስዬ ክስ በከፍተኛ ፍ/ቤት እንዲታይ መከራከሪያ ያቀረቡት ጠበቃ፤ አለበለዚያ ግን ይግባኝ የመጠየቅ የተከሳሽ ህገመንግስታዊ መብትን የሚጥስ ይሆናል ብለዋል፡፡  በፀረ ሙስና አዋጅ የተካተተው አንቀጽ ህገመንግስቱን ስለሚቃረን ለፌዴሬሽን ምክር ቤት ቀርቦ ውሳኔ እንዲሰጥበት የአቶ ስዬ ጠበቃ ቢከራከሩም፤ ፍ/ቤቱ ጥያቄውን ውድቅ ማድረጉ ይታወሳል፡፡
ጥያቄው እንደገና ፍ/ቤት ውስጥ የተነሳው ከአስር አመታት በኋላ የገቢዎችና ጉምሩክ ባለስልጣን ከፍተኛ ሃላፊዎች ላይ ከተመሰረተው ክስ ጋር ተያይዞ ነው፡፡ በአንድ በኩል ዋና ዳሬክተሩ አቶ መላኩ ፈንታ በሚኒስትርነት ማዕረግ የተሾሙ በመሆናቸው፣ በፀረ ሙስና አዋጁ መሰረት ጉዳያቸው በጠቅላይ ፍ/ቤት መታየት ይገባዋል የሚል አስተያየት ቀርቧል፡፡ የፀረ ሙስና ኮሚሽን አቃቤ ህጐች፣ በበኩላቸው ሁሉም ሰው በህግ ፊት እኩል እንደሆነ በህገመንግስት ውስጥ በግልጽ ስለሰፈረ፣ የሁሉም ተከሳሾች ጉዳይ በከፍተኛ ፍ/ቤት መታየት አለበት በማለት ተከራክረዋል፡፡ ፍ/ቤቱም፤ የአዋጁ አንቀፆች ከህገመንግስቱ ጋር እንደሚጋጩ ወይም እንደማይጋይጩ የመወሰንና ለዚህ ክርክር እልባት የመስጠት ስልጣን እንደሌለው በመግለጽ ነው፣ ጉዳዩን ለፌዴሬሽን ም/ቤት ያስተላለፈው፡፡  
በፌደሬሽን ምክር ቤት ስር የተቋቋመው የህገመንግስት ጉዳዮች የአጣሪ ጉባኤ፣ ጉዳዩን ከመረመረ በኋላ የውሣኔ ሃሳብ ያዘጋጀ ሲሆን፣ የምክር ቤቱ አባላት ለበርካታ ሰዓታት ተከራክረውበታል፡፡
“በፀረ ሙስና አዋጅ የተካተተው አንቀጽ ህገ መንግስቱን ስለማይፃረር ባለበት ይቀጥል፤ እንዲያውም ህገመንግስቱን የሚያስከብር ነው” በማለት አስተያየት የሰነዘሩ አባላት፤  “ባለስልጣናት በሙስና ሲባልጉ አምነው የተቀበሉትን ህገመንግስት ስለሚጥሱ ይግባኝ በሌለበት ሁኔታ ፍርዳቸው መታየቱ ተገቢ ነው” ብለዋል፡፡ አንዳንድ የምክር ቤቱ አባላት በበኩላቸው  ጉዳዩ ክብደትና እና ጥልቀት ያለው መሆኑን በመጠቆም ጉዳዩን ለማጤን የተሰጠው ጊዜ አጭር ነው የሚል ሃሳብ አቅርበዋል፡፡
በሌላ በኩል፤ “የይግባኝ መብት የሚጣሰው የአቶ መላኩ ብቻ ሳይሆን የአቃቤ ህግም ነው” በማለት የተከራከሩ አባላት፣ ጉዳዩ በከፍተኛው ፍ/ቤት መታየቱ ሁለቱንም ይጠቅማል ብለዋል፡፡ ይግባኝ በሌለበት ሁኔታ ፍርዳቸው መታየት አለበት በሚል የተሰነዘረውን ሃሳብ በመቃወም  ምላሽ የሰጡት የአጣሪ ጉባኤው አባል አቶ ሚሊዮን አሰፋ “የሚኒስትሮች ክስ ከሌላው ሰው ተነጥሎ ይታይ” የሚል ሃሳብ በዜጐች መካከል የመደብ ልዩነት መኖሩን ከሚያመላክት ፊውዳላዊ አስተሳሰብ የሚመነጭ በመሆኑ ተገቢ አይደለም ብለዋል፡፡
በመጨረሻም፤ አከራካሪው አንቀጽ ህገመንግስቱን ስለሚቃረን ከፀረ ሙስና አዋጅ እንዲሰረዝ በ76 የድጋፍና በ8 የተቃውሞ ድምፅ የተወሰነ ሆን፣ እንዲህ ዓይነቱ ውሳኔ ለምክር ቤቱ የመጀመሪያው መሆኑን በመጠቆም ታሪካዊ ውሳኔ ነው በማለት አፈጉባኤው አቶ ካሳ ተክለብርሃን ተናግረዋል፡፡

Saturday, 28 December 2013 12:28

ሴትና ኪነት

እንደውሀ ሀሳብ እየወረድልኝ ድርሰት መፃፍ ህልም ሆኖብኛል፤በቃ መፃፍ አቅቶኛል! አንድ አመት. . . ሁለት አመት. . . ሶስት አመት. . አምስት አመት. . .  ሙሉ ጠበቅሁ፤  ምንም ነገር ብቅ አላለም- አንድ ገፅ ቃለ ተውኔት መፃፍ እንኳ አልቻልኩም!
ድርሰት መፃፍ አቅቶኝ ማዘኔ ሳያንስ የምወዳት ሚስቴ ሜላት መካሻ ጥላኝ ሔደች!
መለየት እንደዱብዳ ወረደብኝ፡፡ የመፃፍ ችሎታዬ ተሟጦ ከእንግዲህ  መፃፍ እንደማልችል በትያትር ቤት ገምጋሚዎች በተነገረኝ በሁለተኛው ወር ምሽት ላይ ወደቤቴ ስገባ ባለቤቴ ጥላኝ እንደሔደች ተነገረኝ፡፡ ኪነትና ሴት ተመካክረው እስኪመስል ከህይወቴ ሰተት ብለው ወጡ። ኪነትና ሴትን አንድ ላይ ማጣት ልቋቋመው የምችለው አልነበረም። መኖር ራሱ ከዚህ በኋላ ምን ያደርግልኛል? ሰው መኖር ያለበት በምክንያት ነው፡፡ የመኖር ምክንያቶቹ በሙሉ የተወሰዱበት ሰው መኖር ምን ያደርግለታል? ለኔ የመኖር ምክንያቶቼ የነበሩት ሴት እና ኪነት ናቸው. . .  ሁለቱን ከተነጠቅሁኝ በኋላ መኖር ከመተንፈስ የዘለለ አይሆንልኝም፡፡  
ሀያ ስምንት ተውኔት ከፃፍኩ በኋላ በድንገት የመፃፍ ኃይሌን ተቀማሁ፡፡ የመፃፍ ችሎታዬን እንደተነጠቅሁ የተረዳሁት ከግማሽ በላይ ቴአትሮቼን ላሳየሁበት ቴአትር ቤት ያስገባሁት የተውኔት ፅሁፍ በተደጋጋሚ ውድቅ ሲደረግ ነበር።  ለመጨረሻ ጊዜ ግምገማ ሲደረግ፤ ገምጋሚዎቹ የተውኔቱን ፅሁፍ ቀሽምነት የሚያሳዩ ነጥቦችን እያነሱ አስተያየት ሲሰጡ ተሸማቅቄ መግቢያ ሳጣ- በቃ መፃፍ እንደማልችል በግልፅ  ገብቶኝ ነበር።  “መፃፍ አለመቻል ማለት የህይወት መጨረሻ አይደለም!” ብዬ ነበር ለራሴ ደጋግሜ የነገርኩት፡፡
ተሳስቼ ነበር፡፡ መፃፍ ለኔ ህይወት ነበር፡፡ ቃላትን መደርደር የህይወት ምልልሴ ነበር፡፡ ድርሰት ከመፃፍ ውጪ ጫማ ማሰር እንኳ አልችልም፡፡ የተወለድኩት እንድፅፍ ነበር የሚመስለኝ፡፡ በድንገት ግን ብዕሬ አልታዘዝ አለኝ፤ቃላት እንደሰማይ ራቁኝ። ለማን አቤት እንደምል አላውቅም. . . . . .
የመጨረሻውን ቴያትሬን ለግምገማ ሳቀርብ የመሞት ያህል ነበር የተሰማኝ፡፡ ከተውኔት ግምገማው ቢሮ ስወጣ ውስጤ ጭር ብሎ ነበር። በቁሜ የተገነዝኩ ያህል፣የራሴን የቀብር ንፍሮ የቀመስኩ ያህል . . . ድንጋጤ አቅሌን ሰውሮ ጭልም እንዳለብኝ ----ምን ነበር የቴያትር ገምገሚው ያለኝ? የቴያትር ገምጋሚው ንግግር በአእምሮዬ ደጋግሞ ያቃጭልብኛል፡፡ እስከ ህልፈተ ህይወቴ ድረስ በህሊናዬ የሚቀመጥ ንግግር ነበር የተናገረው፡፡
“ህሩይ እርግጠኛ ነህ ይህንን ጽሁፍ አንተ ለመፃፍህ?” ነበር ያለኝ ባለማመን፡፡ በአንገቴ ንቅናቄ ማረጋገጫዬን እንዳገኘ ወደኔ አፍጥጦ እያየ. . .
“ህሩይ ይህ ግምገማ በሁለት አመት ውስጥ ስድስተኛ  ሥራህ ላይ ያደረግነው ነው፡፡ አይገባህም እንዴ? በቃ! የጥበብ አድባር ርቃሀለች! መክሊትህን ጨርሰሀል! እስካሁን በሰራኸቸው እና ተመልካችን አጀብ ባሰኙ ሥራዎችህ እየታወስክ ትኖራለህ፡፡ ከእንግዲህ ግን ሙያ ቀይር! ለወጣቶቹ እድል ስጥ!” ሲል  የራሴን መርዶ ለራሴ ነገረኝ፡፡ ሀያ ስምንት ተውኔቶች ተለምኜ በፃፍኩበት መድረክ ላይ አንድ የሚበቃ ሥራ ማቅረብ አቃተኝ! ኪነት ጨርቄን ማቄን ሳትል ጣጥላኝ ሔዳለች. . . . .እብስ!
እውነቱን ስላላመንኩት ነው እንጂ በቃ መጻፍ አልችልም! አልችልም! አልችልም! ቃላት ያጎርፍልኝ የነበረው ምናቤ ሞቷል!
ለሀያ ምናምን ዓመት ያለማቋረጥ የሰራሁት ሥራ መፃፍ ነው! መፃፍ! መፃፍ! በቃላት ነፍስ መዝራት፤ በቃላት ህይወት መዝራት፤ ከህይወት ህይወትን ቀድቼ ህይወት ላላቸው ህይወትን ማጠጣት፡፡ አሁን ግን የህይወት ምንጬ ደረቀ፡፡ የፈጣሪነት ሚናዬን ተቀምቻለሁ!  ሥራዬ መፍጠር ነበር፡፡ ህይወቴ መፍጠር ነበር፡፡ ነበር፣ነበር፣ነበር. . . . . !!! አንድ የሚረባ ፅሁፍ መፃፍ አቅቶኝ አምስት አመት ተቆጠረ፡፡ መፃፍ እችላለሁ የሚለውን እምነት ይዤ ለአምስት አመት ታገልኩ. . .በቃ መፃፍ አቅቶኛል!
አእምሮዬ ድንገት እንደ ሻተር ዝግት አለ! በፊት በፊት ድርሰት እንዴት ነው የሚመጣልህ? ብለው ሲጠይቁኝ እስቅ ነበር- የአለቃ ገብረሀናን አሽሙር እንደሰማሁ፣የቻርልስ ቻፕሊንን ድምፅ አልባ ቧልት እንዳየሁ ሁሉ በሳቅ ፍርስ እል ነበር፡፡ በምድር ላይ ቀላሉ ሥራ በቃላት ሰዎችን መፍጠር፣እንዲናገሩ ፣እንዲያዝኑ ማድረግ ይመስለኝ ነበር፡፡ ሀያ ስምንቱም ተውኔቶቼ የተዋጣላቸው የሚባሉ ነበሩ፡፡ አምስት አመቴ! ቃላት ከአእምሮዬ መፍለቅ ካቆሙ፣ ቢፈልቁም ጣዕም አልባ ደረቅ ቃላት ናቸው፤ታሪክ በጣቴ በኩል አይመጣም፣ ታሪክ ብዬ የምፅፈው ከተራ ዝብዘባ ያነሰ ነው፡፡ በቃ መፃፍ አልችልም!!
አንድ የማላውቀው ኃይል የድርሰት አቅሜን ነጥቆኛል፡፡ የት ሔጄ አቤት እላለሁ? የትኛው ፍርድ ቤት ይግባኜን ይሰማኛል?
ስለማያስችለኝ ከቴያትር ቤቱ ደጃፍ ላይ ሔጄ ቁጭ እላለሁ፡፡ ከየት መጣ ያላልኩት እንባ አይኔን እየበረቀሰው ወደ ጉንጬ ይንፎለፎላል፡፡ ሰዓሊ ብሩሹ ሲደርቅ፣ቀራፂ መዶሻው ሲወልቅ. . . ምን ይላል? . . . ዘፋኝ ድምፁ ሲጎረንን፣ዳንኪረኛ እግሩ ሲሰበር. . . .  ምን ይሆን የሚሰሩት? እኔ ግን ግራ ገብቶኛል! ህይወት ትርጉም አጥታብኛለች፡፡ ስፅፍ እንዴት ደስተኛ ነበርኩ! ስፅፍ እንዴት ሀሴት አደርግ ነበር!. . . . ንስር የሆንኩ ይመስለኝ ነበር፤ሰማየ ሰማያት በርሬ ቁልቁል ዓለምን ሙሉ የምቃኝ ይመስለኛል፡፡ ሥነ-ፅሁፍ ነፃነቴ ነበር፣ ሥነ-ጽሁፍ ቁልፌ ነበር ከተዘጋ የአስተሳሰብ ሳጥን የምከፈትበት. . . . ሥነ-ፅሁፍ ማዕረጌ ነበር የምጠራበት. . .
የመጨረሻ የተውኔት ፅሁፌ በግምገማ እንዲያልፍልኝ ክፉኛ እንደተመኘሁ ትዝ ይለኛል፡፡ እናቴ በጠና በመታመሟ  ገንዘብ ማግኘት ነበረብኝ። የቤት ኪራይ አለ፣ፋሲካ እየደረሰ ነው. . . ገንዘብ ግን የለኝም ነበር፡፡ ገንዘብ እንዳገኝ የተውኔት ፅሁፍ አዘጋጅቼ ለቴያትር ቤቱ አስገባሁ፡፡ በግምገማ ቅስሜን እንደእንስራ ሰበሩት. . . .ይህ ሁሉ ጫና ኖሮብኝ ከኪነት እና ከሴት አንደኛቸው አብረውኝ ካሉ ጭንቅ አጠገቤ አይደርስም ነበር፡፡ ኪነት እና ሴት በአንድነት ሲርቁኝ ግን. . . .የጨለማ ግድግዳ የከበበኝ ይመስለኛል፡፡
በአንድ ተውኔቴ ውስጥ “ማበድ ሲያንሰኝ ነው!” የሚል ገፀ ባህሪ አለ፡፡ የመፅሀፍ ቅዱሱ ኢዮብን አይነት መከራ የሚደርስበት ይኼ ገፀ ባህሪዬ፤ በመጨረሻ የዓለምን ስቃይ መቋቋም አቅቶት አቅሉን ይስታል-ያብዳል፡፡ ካበደ በኋላ ማበዱን የሚያሞካሽበት ቃለተውኔት አለ።  “ባላብድ ይገርመኝ ነበር! ማበድ ሲያንሰኝ ነው!” ይላል ይህ ገፀ ባህሪዬ፡፡ “እንኳን አበድኩ! በጤነኛ አእምሮዬ ይህንን ሁሉ መከራ አልችለውም ነበር!” ይላል። የራሴን ህይወት እየተነበይኩ ነበር ማለት ነው። አንዴት አንድ የተሳካ ተውኔት መፃፍ ያቅተኛል? ማበድ ሲያንሰኝ ነው! ባብድ ይሻል ይሆን? እብደትን ተመኘሁ. . . .
ከድርሰት ውጪ ሰርቼ ገንዘብ ያገኘሁበት ሥራ ኖሮ አያውቅም! ስለዚህ ዓለም ያለጀንበር መኖር የጀመረች መሰለኝ. . . . .ጨለማ!
የመጨረሻ ተውኔቴ በግምገማ ከወደቀ በኋላ መጠጥ መቀማመስ አዘውትሬ ነበር፡፡ አንድ ቀን ከሰዓት በኋላ የተለመደውን አድርሼ ወደ ቤቴ አቅጣጫ ጉዞ የጀመርኩት. . . . .
11፡00 ሰዓት አካባቢ ይሆናል፡፡ ተማሪዎች ከትምህርት ቤት የሚመለሱበት፣ ፀሀይዋ መስከን የምትጀምርበት፣ሠራተኞች ከሥራ ወደ ቤት የሚቻኮሉበት. . . ጓዳናው ላይ ሰው የሚፈስበት የምወደው ሰዓት ነበር፡፡ በዚህ ሰዓት ጎዳና ላይ መውጣት የድርሰት አምሮቴን ይቀሰቅሰው ነበር። ሰውን የማንበብ ሱስ ነበረብኝ፡፡ ብዙ አይነት ፊቶችን ማንበብ እወድ ነበር... የተከፋ፣ የደነገጠ፣ የተደሰተ፣ የተኮሳተረ፣ የፈገገ፣ የሚቸኩል፣ የተናደደ፣ ተስፋየቆረጠ፣ የተቆጣ፣ የተራበ፣ የተፀፀተ ፊት...፤ በፂም የተከበበ፣ በመነፅር የተጋረደ ፊት፤ ሾካካ፣ መልከቀና፣ የዋህ፣ ጅላጅል ፊት. . . .እነዚህን ፊቶች ማየት ነበር የቃላት ክምር፣ የዓረፍተ ነገር ቋጥኝ ወደ አእምሮዬ የሚያንደረድረው፡፡
ምን ሆኖ  ይሆን ያዘነው? ምን ሆና ይሆን የምትስቀው? ለምን ተፀፀተ?. . .እያልኩ የሰዎችን ፊት ካየሁ በኋላ. . . ወደ መመሰጤ እመጣለሁ --- የፈጠራ ሀሳቦች እየተንከባለሉ ወደ አእምሮዬ ዘው ይሉ ነበር፡፡ የሰው ፊት ነበር መጽሀፌ! የተገለጠ፣ያልተደበቀ፣በብራና ያልተለበጠ፣ነፍስ ያለው መፅሀፍ --- የሰው ልጅ ፊት! እነዚህ ሁሉ ትርጉም ከሰጡኝ አመታት ተቆጥረዋል፡፡ የሰው ፊት ሳይ አፍንጫ እና አይን፣ቅንድብና ጉንጭ፣ከንፈር እና ግንባር. . . ወዘተ ብቻ ናቸው የሚታዩኝ፡፡ ከዛ ውስጥ ያለው የሰው ልጅ ማንነት አይታየኝም. . .ምናቤን ተነጥቄያለሁና፡፡
መፃፍ አቅቶኛል! በዚህ ስሜት ውስጥ ሆኜ ወደ ቤቴ እየሄድኩ ነበር፡፡ በመንገዴ ሙሉ የማስበው ስለተለየችኝ  ኪነት ነበር፡፡ ሚስቴ ያኔ አብራኝ ስለነበረች የኪነትን እጦት መፅናኛዬ እሷ ነበረች፡፡ እሷ ጋ እስክደርስ ግን ስለኪነት አስብ ነበር. . . .
መፍጠር መቻል የሚያስገኘው ደስታን ምናልባት የወለደ ብቻ ያውቀው ይሆናል፡፡ መፃፍ ደግሞ ከዚያ ይበልጣል፡፡ የተወለደ ልጅ ነፍስ ካወቀ በኋላ የራሱን የህይወት ትልም እራሱ ነው የሚኖረው። አማልክቱ ናቸው የተወለደ ልጅን እጣ ፈንታ የሚወስኑት፡፡ በድርሰት ግን ከዚያ በላይ መብት አለ፡፡ ገጸ ባህሪን መውለድ ብቻ ሳይሆን ጥሩና መጥፎ እንዲሆን ማድረግ ይቻላል፡፡ ጥቁር አለያም ቀይ የፊት ቀለም መሥጠት ይቻላል፡፡ የፈጠሩትን ገጸባህሪ እንዲሳካለት ማድረግ ይቻላል፡፡ ደራሲነት የአማልክትን እጣ ፈንታ መጋራት ነው፡፡ እስካሁን ከነበሩ ወላድ እናቶች መካከል የልጁን አንድ ስንዝር አፍንጫ ቁመት የጨመረ የለም፡፡ በድርሰት ውስጥ ግን እነዚህ ሁሉ ይቻላሉ፡፡ የሳምሶን ኃይል ፀጉሩ ውስጥ ነበር፤ የጸሀፊ ደግሞ ምናቡ ውስጥ፡፡ ምናቤን ተቀምቻለሁ. . . በቃ ከእንግዲህ መጻፍ አልችልም!
ይኼን እያሰብኩ ቁልቁል ወደ አትክልት ተራ አቅጣጫ መጓዜን ቀጠልኩ፡፡ ከኋላዬ የሁለት ወጣት ልጃገረዶች ሹክሹክታ ይሰማኝ ነበር፡፡
“አየሽው! ህሩይ ማለት እኮ እሱ ነው፡፡ የዛሬ አምስት አመት በቴሌቪዥን ይታይ የነበረው የህልም ዓለም ሰዎች የሚለውን ድራማ አስታወስሽ? የሱ ደራሲ እኮ ነው፡፡” አለች ተለቅ የምትለው፡፡ የህልም ዓለም ሰዎች በሚል የፃፍኩት ድራማ በጣም ታዋቂ ነበር፡፡
“አረ እኔ አላውቀውም!” አለች አነስ የምትለው
“በተደጋጋሚ መፅሔት ላይ ይወጣ ነበር እኮ! ብዙ ቴያትር ፅፏል!. . .”ትልቅየው ልታስረዳት ሞከረች፡፡
ዞር ብዬ አየኋቸው፡፡ ትልቋ አስራ ስምንት፣ትንሷ ደግሞ አስራ ሁለት አመት ቢሆናቸው ነው፡፡ ትልቋ በአውቅሀለው ስሜት ፈገግ አለችልኝ. . . ትንሷ ደግሞ በእንግዳ ስሜት አየችኝ፡፡ ደነገጥኩ! ለአዲሱ ትውልድ የሚሆን ሥራ የለኝም! በቃ እኔ ታሪክ ነኝ!. .. መፃፍ አልችልም፡፡ ልጆቹን ትቼ ጉዞዬን ቀጠልኩ።
ከሸዋ ሱፐር ማርኬት በሶማሌ ተራ አድርጌ፣ ወደ ሰፈሬ ወደ አሜሪካን ግቢ እስክደርስ ድረስ የሚራመድ ግዑዝ አካል ሆኜ ነበር፡፡ ለወትሮው አሜሪካን ግቢ ስደርስ የሚሰማኝ ሰላም አብሮኝ አልነበረም። የአሜሪካን ግቢ ግርግር፣ልባሽ ጨርቅ የሚሸጡ ወጣቶች ውርውርታ፣በትንንሽ ፔርሙዝ ቡና የሚሸጡ ሴቶች፣የወደቀ የጫት ገረባ የሚበላ ፍየል፣ከመስጂድ የሚመለሱ አባት፣መኪና ላይ የሚጫን ካርቶን፣ ረጅም የብረት ቱቦ በትከሻው ተሸክሞ ”ዞር በሉ! ዞር በሉ!” እያለ የሚያስጠነቅቅ ወጣት፣የተደረደሩ የሊስትሮ ዕቃዎች፣የመስጅድ አዛን፣የራጉኤል ቅዳሴ. . . .አሜሪካን ግቢ የሰው እርሻ ነች፣ሰው ግጥግጥ ተደርጎ የተዘራባት የመርካቶ አዝመራ! አሜሪካን ግቢ የድርሰት ሀድራዬ ነበረች። ሰው ሰው የሚሸት ትንፋሽ የምታሸተኝ. . . ሰው ሰው የሚል ስሜት እንዲሰማኝ የምታደርግ. . . . ከቅርብ አመታት ወዲህ ግን አሜሪካን ግቢ እነዚህን ሁሉ አትሰጠኝም! የማየው ተራ ግርግር ነው! የሰዎች ትርምስ - ምክንያቱም ምናቤን ተቀምቻለሁ!
እንዲህ እያሰብኩ ስሔድ. . . . ከኋላዬ ድምፅ ሰማሁ.. .
“ህሩይ!” ወደ መንደራችን መግቢያ መንገድ ጫፍ ላይ ካለው ሱቅ የተሰማ ድምፅ ነበር-የበድሩ ድምፅ። በተረቡ፣በቀልዱ፣በጨዋታው ቀኔን የሚባርክልኝ በድሩ። መከፋቴን ላጋባበት አልፈለግሁም- ዝም ብዬ ወደ ቤቴ አቅጣጫ መጓዜን ቀጠልኩ፡፡
“ህሩይ ፈልጌህ ነው!” በድሩ ተከትሎኝ ነበር፡፡ አጠገቤ ደርሶ ሁኔታዬን ሲያየው ደስ አላለውም፡፡
“ምን ሆነሀል ህሩይ?” በተጨነቀ ስሜት አስተዋለኝ። ምን ሆንኩ እለዋለሁ? ተዘረፍኩ ልበለው? የመፃፍ አቅሜ ተሟጠጠ፣ቃላት አውላላ ሜዳ ላይ ጥለውኝ እብስ አሉ!.. .ሊገባው አይችልም። እንኳን እሱ የገዛ ጓደኞቼ ችግሬን አውቀውት ምን ፈየዱልኝ?  “ you know what has happened to you? It is a writer’s block. ” እያሉ ለገጠመኝ ጉድ ገለፃ ለመስጠት ነው የሚሞክሩት፡፡ “አሜሪካዊው ደራሲ ፍራንሲስ ስኮት በዚህ በሽታ ይሰቃይ ነበር..   The love of the last tycoon የሚል ድርሰት ጀምሮ እስከህይወቱ ፍፃሜ ሳይጨርሰው ነው የሞተው...” ምናምን እያሉ ነገር ያራቅቃሉ።  እኔ የማውቀው ደስታዬን መነጠቄን ነው! የፀሀፊ መዘጋት የሚባል በሽታ እንደያዘኝ ማወቁ ሳይሆን መድሀኒቱን ነበር የምፈልገው፡፡ ከቃላት የማገኘውን ደስታ ድጋሚ ማግኘት የምችልበትን መንገድ! “ሶደሬ ለሁለት ሳምንት ተዝናና! ወደ ውጪ ሀገር ለምን ቫኬሽን አትወጣም?. . .” የአንዳንድ ሰዎች ምክር ነበር፤በሽታዬ እንዲለቀኝ፡፡ እኔ ግን ደራሲ ነኝ. . . ሶደሬ ለሁለት ሳምንት የሚያስኬድ ገንዘብ ብይዝ እናቴን ነበር የማሳክምበት፡፡
“ባክህ ተወኝ በድሩ! ጥሩ ስሜት ላይ አይደለሁም!” አልኩት፡፡
አንድ ነገር  ሊነግረኝ እንደፈለገ ሲያመነታ ቆየና በእሺታ አንገቱን ነቅንቆ ትቶኝ ሔደ፡፡
ወደ ቤቴ ገባሁ፡፡ ቤት ውስጥ ማንም የለም ነበር፡፡
“ሜላት?” የባለቤቴን ስም ደጋግሜ ጠራሁ፡፡ ምላሽ የለም!
የት ሔደች? ሜላት ከሌለች ቤቱ ሊበላኝ ይደርሳል፡፡ ሜላት ባትኖር በነዚህ አምስት አመታት ውስጥ ምን ልሆን እችል እንደነበር ማሰብ ይከብዳል፡፡ የብዙ ነገር መፅናኛዬ ሜላት ናት! እና እሷን ፈለግሁ. .  የት ሔዳ ነው? በእቅፏ ውስጥ ሆኜ ተስፋ መቁረጤን መርሳት ሻትኩ፣በእቅፏ ውስጥ ሆኜ ዓለምን መርሳት፣በእቅፏ ውስጥ ሆኜ ነገን መርሳት. . .ሜላት የመድሀኒት ያህል ናት ለኔ። በጡቶቿ መካከል አስገብታ፣ በጭኖቿ ደግፋ፣ በተስፋ መቁረጥ የደረሰብኝን ሀዘን የምታስረሳኝ መድሀኒቴ፡፡ . . .እና ክፉኛ ፈለግኋት. . . .
ወደ ሞባይሏ ስደውል ተዘግቷል የሚል ምላሽ አሰማኝ፡፡ በድሩ ትዝ አለኝ፡፡ እሱ ጋ መልዕክት አስቀምጣ ይሆናል፡፡ ወደ በድሩ ሱቅ ፈጠን ብዬ ሔድኩ፡፡
“ህሩይ እንኳን መጣህ! ቤት ልመጣ እያሰብኩ ነበር --- ሜላት መልዕክት ነግራኝ ነበር. . .እዚህ ቆመን ከሚሆን ሻይ ቤት ምናምን ሔደን. . . !” አለኝ። በድሩ ከበድ ያለ ጉዳይ ሲጋጥመው “ሻይ ቤት ሔደን እናውራ” የሚል ልማድ አለው፡፡
“በጣም እቸኩላለሁ! የምን መልዕክት ነው አንተ ጋ ያስቀመጠችው?”  አልኩት ነገሩን ለመስማት ጓጉቼ፡፡
“ትንሽ ጥሩ ነገር አይመስለኝም!. . . . . .” አለና በድሩ አቀርቅሮ ሲያስብ ቆየ፡፡ የፊቱን ጭንቀት ሳይ አንድ ጥሩ ያልሆነ ነገር እንዳለ ገመትኩ፡፡
“ግዴለም ንገረኝ ምንድነው? ሜላት ደህና አይደለችም እንዴ?” አልኩት
“ሜላት ሔዳለች ህሩይ!” አለኝ አንገቱን እንዳቀረቀረ
“የት ነው የሔደችው?”
“የት እንደሄደች ባላውቅም ምናልባት ወደ ክፍለ ሀገር እንደሔደች እገምታለሁ!”
“ለምንድነው የሄደችው? አልነገረችኝም እኮ!. . ” በቁጣ ጠየቅሁት
“አልገባህም ማለት ነው ህሩይ! ጥላህ ሔዳለች እያልኩህ ነው! . . . ላትመለስ ሔዳለች እያልኩህ ነው...” በድሩ እንደእድር ጥሩንባ ነፊ ሞቴን ያወጀ መሰለኝ፤ ከዛ በኋላ ያለውን ንግግሩን አልሰማሁትም። ውስጤ የነበረው ባዶነት እንደጥቁር አዘቅት blackhole/ ጥልቅ ሲሆን ይታወቀኛል- ወሰን አልባ ባዶነት!  
እንደቀፎ ባዶ የሆነ አካሌን እየጎተትኩ ወደ ቤቴ ነበር የተመለስኩት፡፡
ሜላት የወትሮ ፉከራዋ ጥዬህ እሔዳለው የሚል ነበር፡፡ ጨክና ታደርገዋለች የሚል እምነት ግን አልነበረኝም! ፈፅሞ!
ለብዙ ዘመን ፅሁፌ ላይ አተኩሬ ለሴት ልጅ የሚሆን ጊዜ አልነበረኝም፡፡ ሜላትን ካየኋት በኋላ ግን የሴትን ልጅ ውበት ችላ ማለቴን መቀጠል አልቻልኩም፡፡ ውድድ! አደረኳት፡፡ ጓደኞቼ እንኳን “ለረጅም ጊዜ አንድም ሴት ሳታፈቅር የቆየህበትን ጊዜ ለማካካስ ይመስላል” እያሉ ለእሷ ባለኝ ፍቅር ላይ ይቀልዱ ነበር፡፡ እንዲህ እንደምወዳት እያወቀች እንዴት ጥላኝ ትሔዳለች?
“ጠብ የሚል ነገር ለሌለው ለምን ጊዜህን እና ጉልበትህን ታጠፋለህ? ሌላ ሥራ ሞክር! መቀየር አለብን፣መሻሻል አለብን. . . ” ከተጋባን ጀምሮ እንዲህ ነበር የምትለኝ ሜላት፡፡  የእኔ ትልቁ መለያ ደግሞ ለሥጋ ማሰብ አለመቻሌ ነው፡፡ ካልሲ እንኳን ገዝቼ መቀየር የሚከብደኝ አይነት ሰው ነበርኩ፡፡ ሜላት ደግሞ የኔ ተቃራኒ ነበረች። የሚታይ የሚዳሰስ ነገር ትወዳለች፡፡ አዲስ የቤት ዕቃ፣መኪና፣የራሳችን ቤት. . .ቢኖረን የደስታዋ ምንጭ ነው፡፡ ለሷ ስል የቲያትር ቤቶችን መድረክ የሚነቀንቅ ተውኔት ለመፃፍ ደጋግሜ ሞከርኩ. . .ግን አልሆነም! በትዳር በቆየንባቸው አምስት አመታት አብዛኛው የቤት ወጪ የሚሸፈነው ሜላት ሰርታ በምታመጣው ገንዘብ ነበር፡፡ አሁን ግን ሔዳለች . . . .
በቃ ተሸነፍኩ! ሴትንም ኪነትንም በተከታታይ ማጣት ይከብዳል፡፡ የሁለቱም ፍቅር ገላንም ነፍስንም የሚያነድ፣የሚያንገበግብ አቅም ነበረው... “ማበድ ሲያንሰኝ ነው!” የሚለው ገፀ ባህሪዬ እያሽካካ የሚያየኝ ይመስለኛል፡፡ ኪነትንም ሴትንም በተከታታይ እንዳጡ ማወቅ ከባድ ነው. . . .ሴትና ኪነት ኪነትና ሴት. . . . .
ሜላት ጥላኝ እንደሄደች ካወቅሁ በኋላ ነገር ዓለሙ ዞረብኝ፡፡
ጥላኝ በሔደች በሶስተኛው ሳምንት አንድ ተአምር ተፈጠረ፡፡ እስከ ውድቅት ድረስ የቤቴን በር ሳልዘጋ በጨለማ ውስጥ በተቀመጥኩበት፤ ተስፋ መቁረጥ፣ብቸኝነት፣ባዶነት፣መሸነፍ. . . ዙሪያዬን እንደጥንብ አንሳ ይዞሩኝ በጀመሩበት አንድ ተአምር ተከሰተ፡፡ ሴት ብቸኝነትን ማርካ የምትገድል ብርቱ ጦረኛ ኖራለች? እያልኩ ሜላትን ክፉኛ በምፈልግበት ወቅት ተአምሩ መጣ፡፡ ሜላት መሸነፌን የምደበቅባት፣ተስፋ መቁረጤን የምከልልባት ስጦታዬ ነበረች፡፡ ሜላት!ሜላት!ሜላት! ብቸኝነት እንደ ውርጭ ነፍሴን አቆረፈዳት. .  ተስፋ መቁረጤን ማስተንፈሻ ፈለግሁ. . . ሜላት ስላልነበረች ሌላ አማራጭ መፈለግ ነበረብኝ. . .
ለሰአታት ከተቀመጥኩበት ተነስቼ መብራቱን አበራሁ፡፡ ከአልጋው አጠገብ ካለች አነስተኛ ጠረጴዛ ላይ ልሙጥ ነጭ ወረቀት ተቀምጧል፡፡ መፃፊያ እርሳሴን አነሳሁ. . . .
“ባዶ ቤት! ” የሚል ርዕስ ከአእምሮዬ ተስፈንጥሮ ወጣ. . . . . . .
እስኪነጋ ድረስ ከተቀመጥኩበት አልተነሳሁም። ሀሳብ እንደ ጢስ አባይ ፏፏቴ እየተንዶሎዶለ ይጎርፍልኝ ጀመር፡፡ ሁሉን አጣሁ ባልኩበት ሰዓት ኪነት አለሁ ማለቷን ማመን አልቻልኩም፡፡ ለሊቱ ተገባዶ በንጋት ሲተካ በማያቋርጥ የምናብ ጉዞ ላይ ነበርኩ. . .እስከረፋዱ ድረስ ስፅፍ ቆየሁ፡፡ በሰው ተከቦ ብቸኝነት የሚሰማውን አንድ ገፀ ባህሪን መሰረት አድርጎ የሚሔድ የተውኔት ፅሁፍ ነበር፡፡  
እያንዳንዷ ቃል ውስጤን ጠርምሳ ስትወጣ ይታወቀኛል. . . . .በቃ! ከአምስት አመት በፊት እንደነበረው! . . . .የሚወጡት ቃላት እስኪገርሙኝ ድረስ፣የሚፈጠሩት ታሪኮች እስኪያስደምሙኝ ድረስ... .እየፃፍኩት የምጓጓለት ፍሰት ነበረው፡፡ የተሳካ ሥራ እንደሚሆን እርግጠኛ ነበርኩ፡፡ እራሴን በመጀመሪያ ያረካኝ ሥራ በግምገማ ፈፅሞ ወድቆ አያውቅም. . . አምስት አመት ሙሉ ያጣሁት ይኼንን ነበር፡፡ ሀያ ስምንት የመድረክ ጽሁፎቼን ስፅፍ የነበረኝ ስሜት እንደተመለሰ ገብቶኛል፡፡
“ተመልሻለሁ!” ብዬ መጮህ አማረኝ! ወይም እንደአርኬሜደስ “ዩሪካ! ተገኝቷል!” እያልኩ በአሜሪካን ግቢ ውስጣ ውስጥ ሰፈሮች፣በወለኔ ግቢ፣በወልደጋግሬ ግቢ፣በጎርዶሜ ወንዝ፣በጌሾ ጊቢ፣በአባኮራን ሰፈር... ብሮጥ በወደድኩ፡፡ መፃፍ፣መፃፍ. . በቃላት ዓለምን መበርበር. . .
ረፋዱ ላይ ትንሽ ድካም ተሰማኝ፡፡ ከድካሜ በላይ ግን የፃፍኩትን ሳይ ማመን አቃተኝ፡፡ ሀያ አምስት ገፅ ያለምንም ስርዝ ድልዝ ፅፌያለሁ፡፡ በዚሁ ፍጥነት ከሔድኩ በሁለት ቀን ውስጥ የተውኔቱን ፅሁፍ ልጨርስ እችላለሁ፡፡ የማይታመን ነገር ነው! ለእናቴ መታከሚያ ገንዘብ እንደማገኝ ሳስብ ደስታ ሰውነቴን ወረረው፡፡ ጽሁፉን አለፍ አለፍ እያልኩ አነበብኩት. . .አምስት አመት ሙሉ የቆየሁት እንዲህ አይነት ፅሁፍ ለመፃፍ ነበር!
አምስት አመት ሙሉ ግን የት ነበርኩ? እንደ ካዝና ቁልፍ የተዘጋብኝ የኪነት መንገድ እንዴት ሊከፈት ቻለ? እንቆቅልሹ ቅርፅ እየያዘልኝ ሲመጣ አንዳች አስደንጋጭ እውነት ውስጤ ዱብ አለ! ሜላትን ካገባሁ- አምስት አመቴ! የተውኔት ፅሁፍ መፃፍ ካቃተኝ አምስት አመት!
የመፃፍ አቅሜ ጥሎኝ የሔደው ሜላትን መከተል ስጀምር ነበር ማለት ነው! ከሜላት ጋር ከተጋባን ጀምሮ አንድ ተውኔትም ቢሆን መፃፍ አቅቶኛል! እውነቱ ይህ ነበር፡፡ ፈጽሞ ልረዳው ያልቻልኩት እውነት. . . ሜላትን ከማግባቴ በፊት ለረጅም አመት ብቻዬን ነበር የኖርኩት -በወንደላጤነት፡፡ ብሶቴን፣ንዴቴን፣ተስፋ መቁረጤን፣ጉጉቴን የምተነፍሰው በጽሁፍ ነበር፡፡ ኪነት መተንፈሻዬ ነበረች. . . ሜላትን ካገባሁ በኋላ ግን የኪነትን ቦታ ምህረት ወሰደች፡፡ ተስፋ ስቆርጥ በምህረት እቅፍ ውስጥ መግባትን እመርጣለሁ. . . . . ነፍሴ የምትተነፍሰው በሴት እና በኪነት በኩል ነው ማለት ነው. . . . አንደኛዋ ስትመጣ ሌላኛዋ ትሔዳለች. . .ሌላኛዋ ስትሔድ አንደኛዋ ትመጣለች. . . .እኩል መሔድ አይችሉም፡፡ ሁለቱም ሀሳብ ይፈልጋሉ፣ሁለቱም ውበት ይፈልጋሉ፣ሁለቱም ቀናተኞች ናቸው. . ሁለቱም ይናጠቃሉ!
ሜላት ስትሔድ ኪነት መጣች. . . . .
ሜላትን መቼም ማጣት የምፈልግ አይመስለኝም። እስከ ዓለም ዳርቻ ድረስ ሔጄም ቢሆን የምፈልጋት ይመስለኛል. . . ለጊዜው ግን ተውኔቱን መጨረስ አለብኝ። ለእናቴ መታከሚያ የሚሆን ገንዘብ ማግኘት ቅድሚያ የምሰጠው ተግባር ነበር፡፡ወደ ውጪ መውጣቴን ትቼ የተውኔት ጽሁፌን ቀጠልኩ፡፡ ለግማሽ ሰአት ያህል ሀሳቤ ሳይደናቀፍ ስጽፍ እንደቆየሁ የውጪው በር ሲከፈት ተሰማኝ፡፡ ማን እንደመጣ ለማየት ከተቀመጥኩበት ተነስቼ ወደ በሩ እየሄድኩ ሳለ አንድ ሰው ወደ ቤት ውስጥ ገባ- ሜላት መካሻ!
ክው ብዬ ቀረሁ! መፃፊያ ብዕሬ ከእጄ ወደቀ፡፡
ሜላት በቆመችበት እንባዋ በጉንጮቿ እየወረደ በሳግ በታፈነ ድምፅ “አልቻልኩም! ምንም ሳታደርገኝ ጨክኜ ጥዬህ ልሔድ አልቻልኩም!” አለችኝ፡፡ ሜላት ተመልሳ ነበር፡፡ ከሶስት ሳምንት በኋላ . . . .
ተሸክማው የነበረውን የልብስ ሻንጣ ተቀበልኳትና ወደ ጓዳ አስገባሁት፤በቆመችበት ጥምጥም አድርጌ አቀፍኳት፡፡ በከንፈሮቼ እንባዋን መጠጥኩት፤ በከንፈሮቿ ሳመችኝ፡፡ እጅግ አድርጋ ናፍቃኝ ነበር፡፡ ሰውነቴ እንደመንቀጥቀጥ እያደረገው ተንሰፈሰፈ፡፡ ወደ አልጋው ተሸክሚያት ሔድኩ. . . . ልብሷን እስክታወልቅ ትዕግስት አልነበረኝም፤በጭኖቿ ውስጥ ለመደበቅ ተቻኮልኩ፡፡
“እወድሀለው! እወድሀለው!” የሚል ለሆሳስ ቃል ሜላት ታሰማለች፡፡ከገላዋ ተጣብቄ “እኔም እወድሻለሁ!” እላለሁ. . . .የኔ ሴት ሆይ እወድሻለሁ! ላንቺ ያለኝ መውደድ በመስዋዕት የታጀበ ነው፡፡ እናቴን እና ኪነትን መስዋዕት የሚያደርግ መውደድ. . .
ከሴትና ከኪነት ሴትን መርጫለሁ! ሴትን ስመርጥ ደግሞ ሌላ ሴትን አጥቻለሁ. . . . . ሴትና ኪነት፣ ኪነትና ሴት. . . .

“ሰው ለማገልገል መፈጠር መታደል ነው”


ራስዎን ያስተዋውቁ …
ስሜ ጌታቸው ተድላ ይባላል፡፡ አሁን የምኖረው አዲስ አበባ ውስጥ ነው፡፡ ትምህርቴ በእርሻ ኢኮኖሚክስና በገጠር ልማት

ሲሆን የመጨረሻው ማዕረጌ PHD ነው፡፡ በዓለም ዙሪያ ብዙ አገሮች ላይ ሰርቻለሁ፡፡ ጡረታ ስወጣ አገሬ ላይ መጥቼ

መፃፍ የጀመርኩ ሲሆን እስካሁን  ወደ ስድስት ያህል መፃህፍትን ጽፌያለሁ፡፡
የመጽሐፍቱን ስም ቢዘረዝሩልኝ?
የመጀመሪያው መጽሀፌ የአባቴ የእርሻ ሥራ ላይ ያጠነጥናል፡፡ ሁለተኛው መጽሐፍ እኔ ሳልጽፈው ክቡር ፀሐፊ ትዕዛዝ

አክሊሉ ሃብተወልድ (በኃይለስላሴ ጊዜ ጠቅላይ ሚኒስትር የነበሩ ናቸው) እስር ቤት ሆነው የፃፉትን ህዝብ ማወቅ

አለበት በሚል በአማርኛም በእንግሊዝኛም ተረጐምኩት። በመጨረሻም አዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ ፕሬስ “የአክሊሉ

ማስታወሻ” በሚል አውጥቶት በርካታ ቅጂዎች ተሸጠዋል፡፡ ከዚያ በኋላ በራሴ ታሪክ ላይ የሚያጠነጥን “የህይወት

ጉዞዬና ትዝታዎቼ” የሚል መጽሐፍ ፃፍኩኝ። ይህን ከጨረስኩ በኋላ “ተስፋ የተወጠረች ህይወት” የሚል መጽሐፍ

ፃፍኩኝ። በደርግ ጊዜ ስድስት ልጆች ከዘመቻ ጠፍተው ወደ ጅቡቲ ሰባት ቀንና ሰባት ሌሊት የተጓዙበትን ታሪክ

ያሳያል፡፡ በመጨረሻም “ከትዝታ ጓዳ” እና “እንደወጡ የቀሩት ኢትዮጵያዊ” የሚል መጽሐፍ ለመፃፍ በቅቻለሁ፡፡
በተባበሩት መንግስታት ውስጥ ለረጅም ጊዜ መስራትዎ ይታወቃል፡፡ እስኪ የት የት እንደሰሩ ይንገሩኝ…
ከ20 አመት በላይ በተባበሩት መንግስታት የምግብና እርሻ ድርጅት (FAO) ነው የሰራሁት፡፡ በልዩ ልዩ አገሮች ለምሳሌ

በሌሴቶ፣ በታንዛኒያ እና በበርካታ አገሮች ሰርቻለሁ፡፡ ከዚያ በኋላ በአለም የስራ ድርጅት (ILO) ውስጥ ገባሁና

በናይጀሪያ ለአምስት አመት ሰራሁ፡፡ መጨረሻ ላይ በሰላም ማስከበር ሥራ በኢራቅ የሰሜኑ ክፍል (ኩርዶች በሚኖሩበት)

ሁለት አመት፣ ባግዳድ ደግሞ ሁለት አመት በአጠቃላይ ለአራት አመት አገልግያለሁ፡፡ ሳዳም ሁሴን በነበሩበት ዘመን

ማለት ነው።  
ጡረታ ከወጡ በኋላ ከመጽሐፍ ውጭ ምን እየሰሩ ነው?
ከመጽሐፍ ውጭ በአሁኑ ሰዓት በበጐ አድራጊ ድርጅቶች ውስጥ በበጐ ፈቃደኝነት ነው የምሰራው። በዋናነት ሜቄዶንያ

የአረጋዊያንና የአዕምሮ ህሙማን ማዕከል ውስጥ ብዙም ባይሆን የአቅሜን ለማድረግ እየጣርኩኝ እገኛለሁ፡፡
ኢትዮጵያ ውስጥ በወላጅ አልባ ህፃናት፣ በሴቶች ጥቃት፣ በትምህርትና የሴቶችን አቅም በመገንባት ዙሪያ የሚንቀሳቀሱ

የበጐ አድራጐት ድርጅቶች አሉ። እርስዎ ለምን ሜቄዶንያን መረጡ?
ሜቄዶንያን የመረጥኩበት ዋናው ምክንያት የአረጋዊያንና የአዕምሮ ህሙማን ማዕከል በመሆኑ ነው። ብዙ በጐ አድራጐት

ድርጅቶች የሚሰሩት በህፃናት፣ በጉዲፈቻ እና በመሳሰሉት ላይ ነው። ሜቄዶንያ የሚሰራው ስራ በጣም ቅዱስና የተለየ

ነው፡፡ ይህን ስልሽ የሌላው መጥፎ ነው፤ ጥቅም የለውም ለማለት አይደለም። ሜቄዶንያ በትንሽ ብር ብዙ ስራ

የሚሰራበት፣ በጐ ፈቃደኞች ያለ ክፍያና ያለ ደሞዝ፣ ደከመኝ ሰለቸኝ ሳይሉ፣ ሽንትና ሰገራ የማይቆጣጠሩትን ሳይጠየፉ

እያጠቡ እያገላበጡ የሚውሉ የሚያድሩበት ድርጅት ነው፡፡ ይህ በእውነት ልብ የሚነካ በመሆኑ የመረጥኩበት ዋነኛ

ምክንያቴ ነው፡፡ መስራቹ አቶ ቢኒያም በለጠን ውሰጅ… በጣም ወጣት ነው፤ ትልቅ ሰው ነው፤ የሚሰራውም ቅዱስ ስራ

ነው፡፡ ይህን የማይሞከር ስራ ሞክሮ ለዚህ የበቃ ፅኑ ልጅ ነው፤ ይህንን ልጅ ደግሞ ማገዝ አለብኝ በሚል ነው

የመረጥኩት፡፡
እንግዲህ በጐ ፈቃደኛ ሲኮን የግድ ገንዘብ ያለው መሆን አያስፈልግም፡፡ የሜቄዶንያ መስራች  የአቶ ቢኒያም መርህ

“ሰውን ለመርዳት ሰው መሆን በቂ ነው” የሚል ነው፡፡ እርስዎ በየትኛው ዘርፍ ነው እርዳታ የሚያደርጉት?   
እኔ እንግዲህ በተለያዩ ዘርፎች ነው የማገለግለው። በቻልኩት ሁሉ፡፡ ለምሳሌ በአስተዳደሩ በኩል እሰራለሁ። ከእኔ

መሰሎች ጋር ስድስት ሆነን “የአማካሪ ግሩፕ” በሚል ቡድን አቋቁመን የማማከር ስራ እንሰራለን። በገንዘብም በኩል

ቢሆን እውነት ለመናገር ያቅማችንን እያደረግን ነው፡፡ ለምሳሌ ታህሳስ 13 ቀን 2006 ዓ.ም በተደረገው የግሎባል ሆቴል

የገቢ ማሰባሰቢያ ፕሮግራም ላይ ለማሳተም 64ሺህ ብር ያወጣሁበትን “ከትዝታ ጓዳ” እና “እንደወጡ የቀሩት

ኢትዮጵያውያን” የተሰኙ ሁለት መፃህፍቶቼን 900 ያህል ቅጂዎች ለሽያጭ አቅርቤ ገቢ እንዲያገኙበት አድርጌያለሁ፡፡
እኔ ሁለቱን መፃህፍት በመቶ ብር እንዲሸጡ ነበር የተመንኩት፡፡ ነገር ግን እነሱ ሁለቱን በ150 ብር እንሸጣለን ብለው

በዚህ ዋጋ ሲሸጡ ነበር፡፡ ዘጠኝ መቶውም ካለቀ ወደ 135ሺህ ብር ገደማ ያገኙበታል ማለት ነው፡፡ ይህቺ የእኔ ትንሿ

አስተዋፅኦ ናት፡፡
በሜቄዶንያ ከሚገኙ 300 ያህል አረጋዊያንና የአዕምሮ ህሙማን መካከል አይቼው በጣም ስሜቴን ነክቶታል የሚሏቸው

አሉ?
በአጠቃላይ እዛ ያሉት ሁሉ ልብ ይነካሉ፡፡ ነገር ግን እኔም ሆንኩ ባለቤቴ በጣም ልባችንን የነካው አልጋ ላይ ተኝቶ

የሚገኘው ጌዲዮን የተባለው ወጣት ነው፡፡ 24 ሰዓት እዛው እየተገላበጠ ነው የሚውል የሚያድረው። ሰውነቱ ከወገቡ

በታች ፓራላይዝድ ነው፡፡ (በነገራችን ላይ ጌዲዮን በጣም ወጣት፣ ቀይ፣ እጅግ መልከ መልካም ሲሆን መናገር ባይችልም

መስማት ግን ይችላል፡፡ አጠገቡ ያለች በጣም ወጣት አስታማሚና ተንከባካቢው ብቻ የአፉን እንቅስቃሴ አይታ

ትተረጉማለች፡፡ ከዚህ በፊት የሀብታም ቤተሰብ ልጅ ነበር ተብሏል) ይህ ወጣት በጣም ቆንጆና የሚያሳዝን ነው፡፡
አዲስ አድማስ ላይ የወጡት ኮሎኔል ታሪክም ያሳዝናል፤ ነገር ግን አሁን እርሳቸው በጥሩ ሁኔታ ላይ ነው የሚገኙት፡፡

ከሁሉም ከሁሉም ግን ማን ልቤን እንደሚነካው ታውቂያለሽ? የአዕምሮ ህሙማኑ አረጋዊያን እላያቸው ላይ ሲፀዳዱ

ተሯሩጠው የሚያፀዱትና ንፁህ የሚያደርጓቸው አስታማሚዎች ልቤን ይነኩታል። እውነቱን ልንገርሽ እኔ አላደርገውም፡፡

በዚህ መጠን ሰውን ለማገልገል መፈጠር መታደል ነው፡፡ እና እነዚህ በጐ ፈቃደኞች ዝም ብዬ ሳስባቸው ፅናታቸው

ልቤን ይነካዋል፡፡ እግዚአብሔር ይባርካቸው፡፡
ከመፃህፍቱ በተጨማሪ አንድ ስዕል ለጨረታ አቅርበው ነበር አይደል…?
አዎ! “የቴዎድሮስ የመጨረሻው የመቅደላ ጉዞ” የተሰኘ ስዕል ነበረኝ፡፡ ያወጣላቸውን ያህል ያውጣላቸው ብዬ

ሰጠኋቸው፡፡ ከ10ሺህ ተነስቶ መቶ ሺህ ብር ተሸጠ፡፡ በጣም የምወደው እና ሳሎኔ ውስጥ ሰቅዬው የነበረ ስዕል ነው፡፡

ቴዎድሮስ በፈረስ ላይ ሆነው ሰው ከቧቸው ሲጓዙ የሚያሳይ በጣም ማራኪ ስዕል ነው፡፡
ባለፈው እሁድ በግሎባል ሆቴል የተካሄደው የገቢ ማሰባሰቢያ ፕሮግራም አጠቃላይ ድባብ ምን እንደሚመስል

ቢገልፁልኝ…
እውነት ለመናገር … የእሁዱ ፕሮግራም ከጠበቅነው በላይ ነበር፡፡ አንደኛ ከ3500 በላይ ሰው ተገኝቷል። በሁለተኛ ደረጃ

ሁሉም እጁን ዘርግቷል፤ በርካታ ብር ለግሷል፡፡ ለምሳሌ አንድ ስዕል ነበር፡፡ የአንዲት ሴት ስዕል ነው፡፡ ዝም ብሎ ስዕል

ነው፤ አንድ 20ሺህ ብር ቢያወጣልን ብለን ነበር የገመትነው፡፡ ነገር ግን 200ሺህ ብር ተሸጠ። ሌላ ስዕል ደግሞ 50ሺህ

ብር ቢያወጣልን ብለን አስበን 300ሺህ ተሸጠ፡፡ ብቻ ሰው የሜቄዶንያ ስራ ገብቶታል፤ መርዳት አለብን ብሎ አምኗል

ማለት ነው፡፡ ሌላው ስለሜቄዶንያ መታወቅ ያለበት በቀን አንድን ሰው ለመመገብ 20 ብር ያስፈልጋል፤ ለቁርስ፣ ምሳና

እራት ማለት ነው፡፡ አሁን ላሉት 300 ሰዎች በቀን 6ሺህ ብር እናወጣለን፡፡ በወር 180ሺህ ሲሆን በአመት 2 ሚሊዮን

አንድ መቶ ሰማኒያ ሺህ ብር ይወጣል፡፡ ይህ እንግዲህ ለምግብ ብቻ ነው። መድሀኒት፣ ልብስ፣ የንፅህና መጠበቂያ፣ እና

ሌሎችንም ሳይጨምር ነው፡፡ የዛሬ አመት ደግሞ ተረጂዎችን አንድ ሺህ የማድረግ እቅድ አለው፡፡ የሜቄዶንያ ተረጂዎቹ

አንድ ሺህ ሲደርሱ ለምግብ ብቻ ወጭው 20ሺህ ብር በቀን ይሆናል፡፡ በወር 600ሺህ ብር ይመጣል፣ በአመት ደግሞ

ወደ 5.5 ሚሊዮን ይሆናል፡፡ ይሄ ልጅ በእናትና አባቱ ቤት ነው 300ውን እየተንከባከበ ያለው፡፡
ታዲያ ተጨማሪ ቤት ሳይኖር እንዴት አንድ ሺህ ሰዎችን መርዳት ይቻላል?  
ያው መንግስት ሊሰጥ ያሰበውን 20ሺህ ሄክታር መሬት ቶሎ ቢሰጥና እዚያ ትልቅ ቤት ተሰርቶ አረጋዊያን ለብቻ፣

ሴቶችና ወንዶች ለብቻ፣ የአዕምሮ ህሙማን ለብቻ ሆነው፤ ክሊኒካቸዉ እዛው፣ ማረፊያቸውም እንዲሁ ሆኖ የተሻለ ስራ

መስራት ቢቻል ደስ ይለኛል፡፡ ቦታው ይገኝ እንጂ ግንባታው ጊዜ አይወስድም፤ ምክንያቱም ህዝብ ይገነባዋል የሚል

እምነት አለኝ፡፡
በእሁድ ዕለቱ ፕሮግራም በአጠቃላይ ምን ያህል ገቢ አገኛችሁ?
እኔ እስከማውቀው ከሶስት ሚሊዮን ብር በላይ ገቢ ተገኝቷል፡፡ ዲኤክስ መኪናም አግኝተናል፡፡ እግዚአብሔር ይመስገን፡፡
ከጨረታውና ከመሰል ነገሮች እንኳን ከ600ሺህ ብር በላይ ነው የተገኘው። ነገር ግን ወጪው ብዙ ነው፡፡ ያውም

ተጠንቅቀው ነው ገንዘቡን የሚያስተዳድሩት፡፡ ይገርምሻል… ሰው ማኮሮኒ ይዞ ይመጣል፣ ዱቄት ይዞ ይመጣል። በረከቱ

ነው መሰለኝ ተረጂዎቹ ጦማቸውን አድረው አያውቁም፡፡ ቢሆንም አሁንም እርዳታዎቹ ተጠናክረው መቀጠል

አለባቸው፡፡
በመጨረሻ ስለሜቄዶንያና ስለ መስራቹ አቶ ቢኒያም ምን የሚሉት ነገር አለ?
ኦ…ህ ስለ ቢኒያም ለመናገር እቸገራለሁ፡፡ እሁድ ዕለት እንኳን ንግግር ሳደርግ ስሜታዊ ሆኜ ነው ያለቀስኩት፡፡
ቢኒያም የእግዚአብሔር ሰው ነው፡፡ ለእነዚህ የአገር ባለውለታዎችና የአዕምሮ ህሙማን እግዚአብሔር የላከው ሰው ነው፡፡
በእንዲህ አይነት ጊዜ እንዲህ አይነት የተቀደሰ ስራ ለመስራት መመረጥና መታደል ያስፈልጋል። እኛ በእርሱ ዕድሜ

በነበርንበት ጊዜ ድግሪያችንን ይዘን፣ ፔኤች ዲ ይዘን፣ ንብረት አፍርተን፣ ቤት ትዳር ይዘን እያልን ነበር የምናስበው፡፡

እርሱ ግን  እንዴት ጉድጓድ ውስጥ የወደቁትን አንስቼ ያገግሙ እያለ ነው የሚጨነቀው፡፡ ይሄ በእውነት መታደል ነው።

ይህን ወጣት ማንኛውም ሰው ተሯሩጦ ማገዝ አለበት። አቶ ቢንያም እንዳለው “ሰውን ለመርዳት ሰው መሆን በቂ

ነው”፡፡
አመሰግናለሁ።