Administrator

Administrator

           ቱርክ በኢትዮጵያ በኢንቨስትመንቱ ዘርፍ ከፍተኛ መዋለ ንዋይ በማፍሰስ ቀዳሚነቱን ይዛ የቆየችውን ቻይናን በመብለጥ መሪነቱን መረከቧን የኢንቨስትመንት ኤጀንሲን መረጃ በመጥቀስ ወርልድ ቡሊቲን ከትናንት በስቲያ ዘገበ፡፡
በኢትጵዮያ የኢንቨስትመንት ዘርፎች ላይ ቀድመው የተሰማሩት የቻይና ባለሃብቶች እንደሆኑ ያስታወሰው ዘገባው፣ ይሄም ሆኖ ግን ዘግይተው ወደ ኢንቨስትመንቱ የገቡት የቱርክ ባለሃብቶች፣ ሰፋፊ የኢንቨስትመንት ፕሮጀክቶች በመዘርጋት፣ በአገሪቱ ኢንቨስትመንት ከፍተኛ መዋዕለ ንዋይ በማፍሰስ ረገድ በቻይናውያኑ ተይዞ የቆየውን መሪነት ለመረከብ መቻላቸውን ጠቁሟል፡፡
የቱርክ ባለሃብቶች በኢትዮጵያ በተለያዩ የኢንቨስትመንት መስኮች 1 ነጥብ 2 ቢሊዮን ዶላር በማውጣት ቀዳሚነቱን እንደያዙ የጠቆመው ዘገባው፤ ቻይናውያን ባለሃብቶችም ባለፉት አስር አመታት በአገሪቱ 836 ሚሊዮን ዶላር የሚገመት ኢንቨስትመንት መዘርጋታቸውን አስረድቷል፡፡
በተለይ በጨርቃ ጨርቅ ኢንዱስትሪው ዘርፍ በስፋት እየሰሩ የሚገኙት የቱርክ ባለሃብቶች በትላልቅ የኢንቨስትመንት ፕሮጀክቶች ላይ ሲሰማሩ፣ ቻይናውያኑ በበኩላቸው፤ በአብዛኛው በአነስተኛና በብዙ አትላልቅ ፕሮጀክቶች ላይ ተሰማርተው እየሰሩ እንደሚገኙም ታውቋል፡፡
ቱርክ በኢትዮጵያ ኢንቨስትመንት ከፍተኛ መዋዕለ ንዋይ በማፍሰስ ረገድ መሪነቱን ብትይዝም፣ የስራ ዕድል በመፍጠር ቻይና ቀዳሚነቷን ይዛ እንደቀጠለች ጠቅሶ ዘገባው አስታውቋል፡፡ ቻይና በኢትዮጵያ በተሰማራችባቸው የኢንቨስትመንት መስኮች ከ75 ሺ 500 በላይ ለሚሆኑ ሰዎች የስራ ዕድል ስትፈጥር፣ ቱርክ በበኩሏ 20 ሺህ 900 ያህል የስራ ዕድል መፍጠሯን የጠቆመው ዘገባው፤ በአገሪቱ ብዙ የኢንቨስትመንት ፕሮጀክቶችን በማከናወንም ቻይና ቀዳሚነቱን እንደያዘች ገልጿል፡፡
ቻይና 437 ፕሮጀክቶች ሲኖሯት፣ ቱርክ 100 ፕሮጀክቶችን በማንቀሳቀስ ላይ ትገኛለች ብሏል፡፡

የአለማቀፉ ኢንተርኮንቲኔንታል ሆቴሎች አካል ነው

በሆቴል ኢንዱስትሪ ዘርፍ በአለማቀፍ ደረጃ በስፋት በመንቀሳቀስ ከሚታወቁ ታላላቅ ኩባንያዎች አንዱ የሆነው የእንግሊዙ ኢንተርኮንቲኔንታል ሆቴልስ ግሩፕ፣ በአፍሪካ ከከፈታቸው ሆቴሎቹ 30ኛው እንደሚሆን የሚጠበቀውን ክራውን ፕላዛ የተሰኘ ባለ አምስት ኮከብ ሆቴል በአዲስ አበባ እንደሚከፍት ቬንቸርስ አፍሪካ ዘገበ፡፡
የሆቴሉ ባለቤትና ማኔጂንግ ዳይሬክተር አቶ ረዘነ አያሌው በበኩላቸው፣ የሆቴሉ ግንባታ በ18 ወራት ጊዜ ውስጥ ሙሉ ለሙሉ ተጠናቆ አገልግሎት መስጠት እንደሚጀምር ለአዲስ አድማስ ገልፀዋል፡፡
አለማቀፍ ደረጃን የጠበቀው ይህ ዘመናዊ ሆቴል፣ ደረጃቸውን የጠበቁ የመኝታ ክፍሎችን፣ ዘመናዊ ሬስቶራንቶችን፣ መዋኛ ገንዳና ሰባት ግዙፍ የስብሰባ አዳራሾችን ጨምሮ የተለያዩ አገልግሎቶችን የሚሰጡ ክፍሎች ይኖሩታል ተብሏል፡፡
የኢንተርኮንቲኔንታል ሆቴልስ ግሩፕ የህንድ፣ የመካከለኛው ምስራቅና የአፍሪካ ዋና ስራ አስፈጻሚ ፓስካል ጎቪን እንዳሉት፣ በአዲስ አበባ እየተገነባ ያለው ይህ ሆቴሉ በከተማዋ የሚደረገውን በከፍተኛ ሁኔታ በማደግ ላይ ያለውን የቱሪስቶችና የውጭ አገራት ዜጎች ፍሰት ታላሚ ያደረገ ነው፡፡
የሆቴሉ ባለቤትና ማኔጂንግ ዳይሬክተር አቶ ረዘነ አያሌው ለአዲስ አድማስ እንደተናገሩት፣ በአዲስ አበባ ልደታ ኢትፍሩት አካባቢ የሚከፈተው ክራውን ፕላዛ ሆቴል ግንባታ ተጠናቆ የማጠናቀቂያ ሥራዎች እየተከናወኑ ሲሆን፣ ግንባታው በ18 ወራት ጊዜ ውስጥ ሙሉ ለሙሉ ተጠናቆ አገልግሎት መስጠት ይጀምራል ተብሎ ይጠበቃል፡፡የሆቴሉ አጠቃላይ ወጪ ግንባታው ሙሉ ለሙሉ ከተጠናቀቀ በኋላ የሚታወቅ ነው ያሉት አቶ ረዘነ፣ እስካሁን ድረስ የዓለም ባንክ ለግንባታው 19 ሚሊዮን ዶላር ማበደሩን ገልፀዋል፡፡ ሆቴሉ ተጠናቅቆ ስራ ሲጀምር፣ ለበርካታ ዜጎች ሰፊ የስራ ዕድል እንደሚከፍትና እያደገ ለመጣው የአገሪቱ የቱሪስት ፍሰትና ለአለማቀፍ ጉባኤዎች የበኩሉን አስተዋጽኦ እንደሚያበረክትም ተናግረዋል፡፡አለማቀፉ ኢንተርኮንቲኔንታል ሆቴልስ ግሩፕ፣ ሆቴሎቹን ክራውን ፕላዛ፣ ሆሊዴይ ኢን፣ ሆሊዴይ ኢን ኤክስፕረስ፣ ኢንተርኮንቲኔንታልና ስቴይብሪጅ ስዊትስ በተሰኙ አምስት ታዋቂ መጠሪያዎች በተለያዩ የአለም አገራት በመክፈት የሚታወቅ ሲሆን፣ በአሁኑ ወቅት በ12 የአፍሪካ አገራት 29 ሆቴሎች አሉት፡፡

 

በጆን ማክስዌል “The success Journey” በሚል ርዕስ የተፃፈውና በኢ/ር ኢዮብ ብርሃኑ “የስኬት ጉዞ” ተብሎ ወደ አማርኛ የተመለሰው መፅሀፍ ሰሞኑን ለንባብ በቅቷል፡፡
 ስለስኬት መንገዶች መድረሻ፣ ስለ ትክክለኛ የስኬት ምስል፣ ስለ ሀብት፣ ስለስኬትና ስለተሳሳተ ልማዳዊ የስኬት አስተሳሰብ የሚተነትነው  መፅሀፉ፤ በ10 ምዕራፎች የተከፋፈለ ሲሆን በ152 ገፆች ተቀንብቦ በ42 ብር ከ60 ሳንቲም ለገበያ ቀርቧል፡፡  

የሽልማት ስነ-ስርዓቱ መስከረም 24 ይካሄዳል

            በሸገር ኤፍኤም 102.1 የሚተላለፈው የለዛ ፕሮግራም የአድማጮች ምርጫ የሆኑ የመጨረሻዎቹ እጩዎች ተለይተው መታወቃቸውን አዘጋጆቹ ገለፁ፡፡ ለሁለት ወራት ያህል በwww.shegerFM.com እና yahoonoo.com ላይ አድማጮች ለአርቲስቶች ድምፅ ሲሰጡ መቆየታቸውን የገለፁት አዘጋጆቹ፤ 60 በመቶ በአድማጮች፣ 40 በመቶው በባለሙያዎች በሚሰጥ ውጤት አሸናፊዎች ታውቀዋል ብለዋል፡፡
በ “ምርጥ ወንድ ተዋናይ” ዘርፍ ግሩም ኤርሚያስ በ “ጭስ ተደብቄ” ፊልም፣ ይስሃቅ ዘለቀ በ “ቀሚስ የለበስኩ’ለት”፣ መሳይ ተፈራ በ“ትመጣለህ ብዬ”፣ ሚካኤል ሚሊዮን በ“አይራቅ”፣ ታሪኩ ብርሃኑ በ“ህይወትና ሳቅ” እና ሰለሞን ቦጋለ በ“ሶስት ማዕዘን” ፊልሞች የመጨረሻዎቹ እጩዎች ሆነዋል፡፡
በ “ምርጥ ሴት ተዋናይ” ዘርፍ፣ ድምፃዊት ዘሪቱ ከበደ በ“ቀሚስ የለበስኩ’ለት”፣ ሰላማዊት ተስፋዬ በ “በጭስ ተደብቄ”፣ ማህደር አሰፋ በ“አይራቅ”፣ ሩታ መንግስተአብ በ“ረቡኒ”፣ ማህደር አሰፋ በ“ህይወትና ሳቅ” እንዲሁም ማህደር አሰፋ በ “ዘውድና ጎፈር” የመጨረሻዎቹ እጩዎች ሊሆኑ ችለዋል፡፡
ዘንድሮ ለአራተኛ ጊዜ በሚካሄደው በዚህ የአድማጮች ምርጫ ላይ አምስት ፊልሞች በአድማጮች የተሻለ ነጥብ ያገኙ ሲሆን ፊልሞቹም “በጭስ ተደብቄ”፣ “ትመጣለህ ብዬ”፣ “ህይወትና ሳቅ”፣ “ቀሚስ የለበስሉ’ለት”፣ “አይራቅ” እና “ረቡኒ” መሆናቸው ታውቋል፡፡ በምርጫው ላይ ምርጥ አልበሞች የተካተቱ ሲሆን የብዙአየሁ ደምሴ “ሳላይሽ”፣ የስለሺ ደምሴ “ያምራል ሀገሬ”፣ የአስቴር አወቀ “እወድሃለሁ”፣ የሚካኤል ለማ “ደስ ብላኛለች”፣ የአብርሃም ገ/መድህን “ማቻ ይሰማኒሎ” እና የተመስገን ገ/እግዚአብሔር “ኮራሁብሽ” ተመርጠዋል፡፡ በምርጥ ነጠላ ዜማም የሙዚቃ ቪዲዮ ዘርፍ ደግሞ መካከል የጃኪ ጎሲ “ፊያሜታ፣ አስቴር አወቀ የተሳፈችበትና በ“የኛ” የተሰራው “ጣይቱ”፣ የበሃይሉ አጎናፍር “አዩ እሹሩሩ”፣ የናቲ ማን “ጭፈራዬ” እና የተመስገን ገ/እግኢዘብሔር “ኮራሁብሽ” በመራጮች ልቀው መገኘታቸውን አዘጋጆቹ ተናግረዋል፡፡
በምርጥ ነጠላ ዜማ ዘርፍ የግርማ ተፈራ “መቼ ትመጫለሽ”፣ የበሃይሉ አጎናፍር “አዩ እሹሩሩ”፣ የጃኪ ጎሲ “ፊያሜታ”፣ የዘሪቱ ከበደ “የወንድ ቆንጆ”፣ የአቤል ሙሉጌታ “ልብ አርማ አመት” እና የ “እኛ” እና የአስቴር አወቀ ስራ “ጣይቱ” በአድማጮች ከፍተኛ ነጥብ አግኝተዋል ተብሏል፡፡ በሽልማት ዘርፍ ውስጥ አዳዲስ ድምፃዊያን በእጩነት የቀረቡ ሲሆን ሚካኤል ለማ፣ ተመስገን ገ/እግዚአብሔር፣ እመቤት ነጋሲ፣ አዩ አሳዬኝ አለሙና ዳንኤል ፍስሃዬ የመጨረሻ እጩ ሆነው ተመርጠዋል፡፡
የድምፅ መስጠት ሂደቱ በቀረቡት የመጨረሻ ዙር እጩዎች ላይ ለቀጣዩ 30 ቀናት ከተካሄደ በኋላ አሸናፊዎች መስከረም 24 ቀን 2007 ዓ.ም በጣሊያን ካልቸራል ኢንስቲትዩት በሚካሄድ የቀይ ምንጣፍ የሽልማት ስነ-ስርዓት ላይ ይሸለማሉ ተብሏል፡፡
 በሽልማት ስነ-ስርዓቱ ላይ የፒያኖ ባለሙያው ግርማ ይፍራሸዋን ጨምሮ በርካታ ሙዚቀኞች ስራዎቻቸውን በማቅረብ የሽልማት ስነ-ስርዓቱን ያደምቃሉ ተብሏል፡፡          

የኒውዮርክ ታይምስ መጽሔት “From Chopin to Ethiopia and Part way Back Again (“ከቾፐን እስከ ኢትዮጵያ እና ደርሶ መልስ”) በሚል ባስነበበው የሙዚቃ ቅኝት ስቲቭ ስሚዝ ስለግርማ ይፍራሸዋ ያሰፈረው በከፊል ይሄን ይመስላል፡-
 “…በተነፃፃሪ ሲታይ፤ ስለክላሲካል ሙዚቃ በአፍሪካ፤ የሚያመላክቱ ጥቂት ማረጋገጫዎች ብቻ ይኑሩ እንጂ የምዕራቡ ክላሲካል ባህል በሌላው ዓለም ማለትም ከቬኔዝዌላ እስከ ቻይና እንደተንሰራፋው ሁሉ የአፍሪካንም ዙሪያ መለስ ማዳረሱ ገሀድ ነው፡፡ ለዚህ አስረጅ የሚሆነን የ45 ዓመቱ ኢትዮጵያዊ ፒያኒስትና ቀማሪ ግርማ ይፍራሸዋ በብሩክሉን “ኢሹ ፕሮጀክት ሩም” ቅዳሜ ምሽት ያቀረበው ምርጥ የፒያኖ ሥራ፤ እጅግ ብርቅ፣ ሥነ ውበታዊና ተምሳሌታዊ የክላሲካል ሙዚቃ መናኸሪያ መሆኑን የሚያሳይ ነው!
…. ግርማ “የኢትዮጵያዊያን በገና” ሊባል በሚችለው በክራር ነው የሙዚቃ ልጅነቱን የጀመረው፡፡ አዲስ አበባ ሙዚቃ ት/ቤት ሲገባ ከፒያኖ ጋር ተገናኘ፡፡ ከዚያ ነው በነቃ አዕምሮው በቡልጋሪያ የሶፊያ ስቴት ኮንሰርቫቶሪ መደበኛ ትምህርቱን ገፍቶ የተካነው…
“… ወደ ኢትዮጵያ በ1995 እ.ኤ.አ ከተመለሰ በኋላ ግርማ ደረጃውን የጠበቀ ክላሲካል ትርዒት ምን እንደሚመስል ደርዝ ያለው ግንዛቤ ማስጨበጥን ሥራዬ ብሎ ከመያያዙ ሌላ፤ አዳዲስ የሙዚቃ ስራዎችን ፅፏል፡፡ ለነዚህ አዳዲስ የጥበብ ስራዎች መቀመሪያ ይሆነው ዘንድ የአውሮፓን የጥበብ መላ ከኢትዮጵያ ሙዚቃና ሥነ-ትውፊታዊ ዕሴት ጋር በማጋባት ተጠቅሟል፡፡....››


ከፍተኛ ሽያጭ ያስመዘገበው አዲሱ አልበሙ በአሜሪካ በቢልቦርድ ሰንጠረዥ 23ኛ ደረጃ አግኝቷል ታዋቂው ፒያኒስት ግርማ ይፍራሸዋ በቅርቡ በአሜሪካ ያስመረቀው “Love and peace” የተሰኘ አዲስ አልበሙ፤ በቢልቦርድ ሰንጠረዥ 23ኛ ደረጃ ላይ እንደተቀመጠለት ይናገራል፡፡ በአሜሪካ ያቀረበው ኮንሰርት እንደተወደደለት የገለፀው ፒያኒስቱ፤ ኒውዮርክ ታይምስ ጋዜጣ በአድናቆት የተሞላ ጽሑፍ እንዳወጣለት ጠቁሟል፡፡ የአዲስ አድማስ ጋዜጠኛ ኤልሳቤት ዕቁባይ ከግርማ ይፍራሸዋ ጋር ያደረገችው ቃለምልልስ እንዲህ ቀርቧል፡፡ ወደ ሙዚቃ እንዴት እንደገባ በመናገር ይጀምራል፡-  


ሙዚቃ የጀመርኩት በልጅነቴ ክራር በመጫወት ነው፡፡ ክራር ስጫወት ነው ያደግሁት፡፡ ፡፡ሙዚቃን በሳይንሳዊ መንገድ ለማጥናት ደግሞ  ያሬድ ሙዚቃ ትምህርት ቤት በመግባት፤ ከባህል ክራር፣ ከዘመናዊ ደግሞ ፒያኖን ለአራት አመት ተማርኩ፡፡ የያሬድ ሙዚቃ ትምህርት ቤት ትምህርቴን እንዳጠናቀቅሁ፣  በ1980 ስኮላርሺፕ አግኝቼ ወደ ቡልጋሪያ  አቀናሁ፡፡
እዚያ ከሄድክ በኋላ ግን ችግር ገጠመህ…
ፒያኖ ለመማር አልሜ ቡልጋሪያ በሚገኝ የሙዚቃ አካዳሚ ለሁለት አመት ከተማርኩ በኋላ በወቅቱ  በተፈጠረው የሶሻሊስት ካምፕ መፍረክረክና መፍረስ   ሳቢያ  የእኔና  በሙዚቃ ትምህርት ቤቱ የነበሩ ሌሎች ተማሪዎቸ እጣ ፈንታ ስደት ሆነ፡፡ ሁሉም በየፊናው ሲበተን እኔ  ጣሊያን ስደተኞች ካምፕ ውስጥ ገባሁ፡፡ ለስድስት ወራት ያህል  “ክርስቲያን ብራዘርስ” የተባሉ በጎ አድራጊዎች እየረዱኝ በካምፑ ተቀመጥኩ፡፡ ካምፑ ውስጥ ያሉ የተለያዩ አገር ስደተኞች በሞሉት ፎርም ላይ አሜሪካ ወይም ካናዳ መሄድ እንደሚፈልጉ ሲያሰፍሩ፣ እኔ  ግን ትምህርቴ  ለምን እንደተቋረጠ በመግለፅ የፒያኖ ትምህርቴን ቡልጋሪያ ሄጄ መቀጠል እንደምፈልግ ገለፅኩ፡፡ የበጎ አድራጎት ድርጅቱም የኔን ጥያቄ ከሌሎች በመለየት ነገሮች ሲረጋጉ የትምህርት ክፍያውን እየከፈሉ ትምህርቴን እንድጨርስ ቡልጋሪያ  መልሰው ላኩኝ፡፡ በአጠቃላይ ሰባት አመት የፈጀውን የፒያኖ ትምህርቴን አጠናቅቄ ማስተርሴን ካገኘሁ በኋላ ተመልሼ ጣሊያን ሄድኩ፡፡
ትምህርቴን እንድጨርስ የረዳኝ ድርጅት አሮጌ ፒያኖ ቢሰጠኝ እያልኩ እመኝ ነበር፡፡ ጣሊያን አገር በቆየሁበት ጊዜ ኮንሰርት ሰርቼ ስለነበር እሱን ተከትሎ ድርጅቱ አዲስ ፒያኖ በሽልማት ሰጠኝ፡፡ አሮጌ ቢሰጡኝ እያልኩ ስመኝ ፋብሪካ ድረስ ሄጄ መርጬ ባለፒያኖ ሆንኩ፡፡ ያ ለኔ ትልቅ ደስታ ነበር የፈጠረልኝ፡፡
ፒያኖዋ ግን ሌላ ስጋት ይዛ መጣች…
አዎ ፒያኖዋ በአውሮፕላን ከኔ ቀደም ብላ ነበር አዲስ አበባ የገባችው፡፡ እኔ ከመጣሁ በኋላ ፒያኖዋን ለመውሰድ ስጠይቅ፣ የቅንጦት እቃ ስለሆነ ታክስ መክፈል አለብህ በሚል ሁለት ወር ተያዘች፡፡ ሁለት ወር ሙሉ በየቀኑ አየር መንገድ እመላለስ ነበር፤ ምክንያቱም ፒያኖዋ የተቀመጠችው ደጅ ላይ ስለሆነ ፀሀይና ዝናብ እንዳያበላሻት በየቀኑ እየሄድኩ የምትሸፈንበትን ላስቲክ አስተካክላለሁ፣ እቀይራለሁ፡፡ እዚያ አካባቢ ያሉ ሰዎች እንዲንከባከቡልኝም አደራ እላለሁ፡፡ በመጨረሻ የጣሊያንና የቫቲካን ኤምባሲዎች ጣልቃ ገብተው በስጦታ እንደተሰጠኝ ለኢትዮጵያ መንግስት በደብዳቤ አሳውቀውልኝ እጄ ገባች፡፡ ፒያኖዋን ስረከብ ገልጬ ሳያት ከወገቧ በታች ዝናብ ገብቶባታል፡፡ በጣም አዘንኩና አለቀስኩ፡፡ በአካባቢው የነበሩ ሰዎች ለምን እንደማለቅስ ግራ ገባቸው፤ አንዳንዶች ደግሞ ለእንጨት ያለቅሳል እንዴ ብለውኛል፡፡ በነገርሽ ላይ ይህ ታሪክ የእንግሊዝ መንግስትና አዲስ አበባ የሚገኘው የእንግሊዝ ኤምባሲ፣ ለኢትዮጵያ ሚሊኒዬም  በጋራ ባወጡት ትልቅ መፅሀፍ ውስጥ ከተካተቱ ታሪኮች አንዱ ነው፡፡
ክላሲካል ሙዚቃ ምን አይነት ሙዚቃ ነው? እኛ አገር በመሳሪያ ብቻ ከተቀነባበረ ሙዚቃ ጋር የመቀላቀል ነገር ይስተዋላል…
የክላሲካል ሙዚቃ በ17ኛው ክፍለ ዘመን የተጀመረ የሙዚቃ ስልት ሲሆን በረጅም ጊዜ የትምህርት ሂደት የሚገኝ የሙዚቃ ክህሎት ነው፡፡ ክላሲካል ሙዚቃን በልምድ መጫወት አይቻልም፡፡ የክላሲካል ሙዚቃ ተብሎ ሲነሳ  እነ ሞዛርት፣ ሀይደን፣ ቤትሆቨን የመሳሰሉት የሰሯቸው ስራዎች ይጠቀሳሉ፡፡
እኛ አገር ያለው የክላሲካል ሙዚቃ ተቀባይነት ምን ይመስላል?
አድማጭ አለው፤ አቅርቦት ግን የለም፡፡ ፒያኖ ማግኘት እጅግ በጣም ከባድ ነው፡፡ በዚህ የሙዚቃ ዘርፍ መውጣት የሚፈልጉ ብዙ ልጆች አሉ፤ ግን የክትትል ችግር አለ፡፡ ቅድም እንዳልኩሽ የረጅም ጊዜ ስልጠና ይፈልጋል፡፡ ኢትዮጵያ ውስጥ ተሰጥኦ ያላቸው ልጆች አሉ፡፡ እነሱን የሚፈልጉበት ለማድረስ ግን ብዙ ክትትል እና ድጋፍ ይፈልጋል፡፡
ያሬድ ሙዚቃ ትምህርት ቤት ማስተማሩን ለምን ተውከው?
እንዳልኩሽ ማስተማሩ በጣም ጊዜ ይጠይቃል፡፡ እኔ ደግሞ አጫጭር ኮርሶችን ስከታተልና ኮንሰርቶች ማሳየት ስጀምር፣ ቁጭ ብሎ የማስተማሩን ስራ እንዳያስተጓጉል በማለት ነው የተውኩት፡፡
 ቡልጋሪያ አስተማሪህ የነበሩትን ፕሮፌሰር አንተ በምታስተምርበት ያሬድ ሙዚቃ ትምህርት ቤት ኮንሰርት እንዲያሳዩ አድርገህ ነበር፡፡ እስቲ ስለሱ ንገረኝ…
ለእኔ እዚህ መድረስ የቡልጋሪያ አስተማሪዬ ፕሮፌሰር ኢታናስ ኮርቴሽ ትልቅ አስተዋፅኦ አድርጓል፡፡ እንደመምህሬ ሳይሆን እንደ ወላጄ ነው የማየው፡፡ እሱን ኢትዮጵያ አምጥቶ ኮንሰርት እንዲያሳይ ማድረግ ደግሞ የረጅም ጊዜ ህልሜ ነበር፡፡ በ2011 የሀንጋሪያዊው አቀናባሪ የፍራንስ ሊስታ 200ኛ አመት በአለም አቀፍ ፌስቲቫሎች ይከበር ስለነበር፣ ይህን አጋጣሚ ተጠቅሜ፣ እዚህ አገር ያሉትን የዲፕሎማቲክ ማህበረሰብ አግባብቼ ፕሮፌሰሩ አዲስ አበባ መጥቶ ኮንሰርት እንዲያቀርብ ጠየቅሁና ተሳካ፡፡ ኮንሰርቱም ተሰራ፡
አንተም ባለፈው ጥር ቡልጋሪያ በተማርክበት አካዳሚ ኮንሰርት አቅርበሃል…
አዎ፡፡ ከዚያም በተጨማሪ በቫዮሊን፣ በቼሎ እና በሌሎች የሙዚቃ መሳሪያዎች አዲስ ስራ ሰርቻለሁ፡፡ ቡልጋሪያ የሄደኩት እሱን ለማስቀረፅ ነበር፡፡ የተማርኩበት አካዳሚ ውስጥ በጥሩ ሁኔታ ተቀረፀ፡፡ ከዚያ እዚህ ያደረሰችኝን ቡልጋሪያን ኮንሰርት ሰርቼ ላመስግናት አልኳቸው፡፡ በጣም ደስ አላቸውና ኮንሰርቱን ሰራሁ፡፡ እነሱ የኔን የሙዚቃ እድገት እያንዳንዷን ደረጃ ይከታተሉ ነበር፡፡ ከኮንሰርቱ በኋላ “ቡልጋሪያን በተለያዩ የአለም መድረኮች እያስጠራህ ነው” ብለው  ትልቅ ሙያተኛና አስተዋፅኦ ላደረጉ ሰዎች የሚሰጠውን ከፍተኛ ሜዳሊያ ሸለሙኝ፡፡ በአሜሪካን በ2010 ዓ.ም ላይ  ትልቅ ኮንሰርት ተደርጎ ተሳትፌ ነበር፡፡ ሁለት የአሜሪካ ዩኒቨርሲቲዎች በሙዚቃ ዲፕሎማሲ የክብር እውቅና ሰጥተውኛል፡፡
የአሜሪካኑ የአልበም ማስመረቅ ፕሮግራም እንዴት ነበር?
የአሜሪካኑ ፕሮግራም  በጣም ውጤታማ ነበር፤ እንደምታይው ደስታው እስከአሁን ከፊቴ ላይ አልጠፋም፡፡ ሂደቱ ከተጀመረ ቆይቷል፡፡ “ኤምሲል ዎርልድ ሪከርድስ ሌብል”  በሚል የተባለ ኩባንያ ነው፡፡ ጥሩ ስራ የሰሩ ታዋቂ ሰዎችን ማስተዋወቅ ሲሆን ትልቁ ስራቸው ግን ያልታወቁ ሰዎችን መፈለግና ማስተዋወቅ ነው፡፡ “ስራህን በኢንተርኔት ላይ አይተነዋል፤ ጥሩ ነው እናስተዋውቅህ” ቢሉኝም ብዙዎች እንደዚያ እያሉ ተግባራዊ ስለማያደርጉት  አላመንኳቸውም ነበር፡፡ በኋላ ግን ስራዎቼን በአዲስ እንድቀርፅና ኮንሰርት እንዳደርግ የሚያስችል የስራ ፈቃድ እና ቪዛ ላኩልኝ፡፡ በ2013 ሄጄ ኮንሰርት አቀረብኩ፤ ስራዬንም ቀረፅኩ፡፡ በወቅቱ ኒውዮርክ ታይምስ ጋዜጣ በአድናቆት የተሞላ ፅሁፍ አወጣ፡፡ ሞራሌን በጣም ከፍ አደረገው፡፡ ከአንድ አመት በኋላ፣ ሰሞኑን ማለት ነው ሲዲዬን ለቀቅኩ፡፡ የአልበሙ መጠሪያ “ላቭ ኤንድ ፒስ” ነው፡፡ አልበሙ  ከፍተኛ ሽያጭ ነው ያስመዘገበው፡፡ በአሜሪካ የሙዚቃ ደረጃ በሚያወጣው የቢልቦርድ ሰንጠረዥም 23 ደረጃ ላይ ነበር፡፡ ከዚህ በፊት ከአርቲስት ሚካኤል በላይነህ ጋር የሰራሁት “መለያ ቀለሜ” የሚለው አልበምም በቢልቦርድ ሰንጠረዥ የገባ ሲሆን ለብቻዬ ከሰራኋቸው ውስጥ ግን የአሁኑ የመጀመሪያዬ ነው፡፡
የአሜሪካው ኮንሰርት ብዙ ኢትዮጵያውያን ታድመውት ነበር?
ብዙ ባይሆኑም ነበሩ፡፡ እንዲያውም ከኮንሰርቱ በኋላ እራት ጋብዘውኝ እንዴት አናውቅህም አሉኝ፡፡ ከጋባዦቼ አንዱ ደግሞ “አንተን የሙዚቃ ግርማ ሞገስ ብዬሀለሁ” አሉኝ፡፡ ይህ አባባል ለኔ ትልቅ ትርጉም አለው፡፡ አባቴ አስራ ሁለተኛ ክፍል ጨርሼ ዩኒቨርሲቲ ከተማርኩ በኋላ ወደ ስራ እንድገባ ነበር የሚፈልገው፡፡ የሙዚቃ ጉዞውን እንዳታደናቅፉት ብለው ብዙ እገዛ አድርገው ለዛሬ እኔነቴ የለፉት አጎቴ ናቸው፤ ስማቸው ደግሞ ሞገስ ነው፡፡ ግርማ ሞገስ ሲሉኝ በጣም ደስ አለኝ፡፡
ልጆችህን ፒያኖ እያስተማርክ ነው?
አዎ! የትምህርት ጊዜያቸውን ሳልሻማ በትርፍ ሰአት አስተምራቸዋለሁ፡፡
በሚቀጥለው ሐሙስ አዲስ አመት ነው፡፡ መጪውን  አመት እንዴት ትቀበለዋለህ?
እንግዲህ እድሜ አግኝቶ  አዲስ አመትን መቀበል  ትልቅ ነገር ነው፡፡ በተቻለ መጠን አዳዲስ ስራዎቼን እንዲሁም ተሰርተው የተቀመጡትን የማስተዋውቅበት አመት ይሆናል፣ ሌሎች ብዙ በሮችም ይከፈታሉ ብዬ በተስፋ እቀበለዋለሁ፡፡

          የአፍሪካ ዋንጫ ለማዘጋጀት  ጊዜው የኢትዮጵያ እንደሆነ ሱፐር ስፖርት ዘገበ፡፡ የኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌደሬሽን ሊቢያን በመተካት በ2017 እ.ኤ.አ ላይ 31ኛው የአፍሪካ ዋንጫን ለማስተናገድ እንደሚፈልግ ያስታወቀው ከ2 ሳምንታት በፊት ሲሆን በኦፊሴላዊ ደረጃ ለካፍ ማመልከቻ ስለማስገባቱ ግን የታወቀ ነገር የለም፡፡ የአፍሪካ እግር ኳስ ኮንፌደሬሽን  ሊቢያን በመተካት  አዘጋጅነቱን ለሚያመለክቱ አገራት የሰጠው የግዜ ገደብ  3 ሳምንታት ይቀሩታል፡፡ ኢትዮጵያ አመልክታ ተቀባይነት ካገኘች ለ4ኛ ጊዜ የምታስተናግደው የአፍሪካ ዋንጫ ይሆናል፡፡
ከዚህ ጋር በተያያዘ በወጡ ዘገባዎች ኢትዮጵያ የአፍሪካ ዋንጫ መስራች እንደነበረች በማስታወስና ባለፉት 3 ዓመታት ለ31 ዓመታት ከውድድሩ የራቀችበትን ሁኔታ በቀየረ የእግር ኳስ ለውጥ ላይ እንደምትገኝ በመግለፅ አዘጋጅነቱን ብታገኝ ይገባታል ብለዋል፡፡ ከሁለት ሳምንት በፊት በአፍሪካ የኢኮኖሚ፤ የፖለቲካ እና ዓለም አቀፍ ዲፕሎማሲ መናሀርያነት የምትጠቀሰው  ኢትዮጵያ የአፍሪካ ዋንጫን ለማዘጋጀት ፍላጎት እንዳላት ገልፆ የዘገበው ቢቢሲ ነበር፡፡ በወቅቱ በአዲስ አበባና  በባህርዳር  ሁለት ዝግጁ ስታድዬሞች መኖራቸውን ለቢቢሲ የተናገሩት የኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌዴሬሽን ፕሬዚዳንት አቶ ጁነዲን ባሻ ሲሆኑ ፤ በሌሎች የአገሪቱ ክልሎች ደረጃቸውን የጠበቁ ስታድዬሞች ግንባታ እየተጠናቀቀ መሆኑን በመጥቀስ ውድድሩን ለማስተናገድ ዝግጁ ነን ብለዋል፡፡ ኢትዮጵያ የፊፋ እና የኦሎምፒክ ስታንዳርድን የሚያሟላ እና 60ሺ ተመልካች የሚያስተናግድ ብሄራዊ ስታድዬም በአዲስ አበባ ለመስራት እቅድ እንዳላት የገለፀው የሱፕር ስፖርት ዘገባ ሶስት አፍሪካ ዋንጫዎችን ያስተናገደው የአዲስ አበባው ብሄራዊ ስታድዬምም ከፍተኛ እድሳት ተደርጎለት ለመስተንግዶ ሊደርስ እንደሚችል ጠቅሷል፡፡
በ2017 እኤአ ላይ 31ኛውን አፍሪካ ዋንጫ እንድታዘጋጅ  ተመርጣ የነበረችው ሊቢያ  መስተንግዶውን የተወችው በአገሪቱ በቂ ሰላምና መረጋጋት አለመስፈኑ በፈጠረባት እክል እንደሆነ ያስታወቀችው ከሶስት ሳምንት በፊት ነበር፡፡ ይህን ተከትሎ የአፍሪካ እግር ኳስ ኮንፌዴሬሽን ካፍ ባወጣው መግለጫ  እንዳመለከተው ሊቢያ ለውድድሩ የሚያስፈልጉ ስታድዬሞችን በመገንባት እንደማይሳካላት እና በአስተማማኝ ፀጥታ ውድድሩን ለማካሄድ እንደማትችል አረጋግጫለሁ በማለት ለአባል ፌደሬሽኖቹ ምትክ አዘጋጅን ለማግኘት ጥሪ አቅርቧል፡፡
ሱፕር ስፖርት  ጊዜው ኢትዮጵያ የአፍሪካ ዋንጫን የምታዘጋጅበት ነው በሚል ርእስ በሰራው ዘገባ በኢትዮጵያ ስፖርት ዙርያ ባሉ ባለድርሻ አካላት የተሰጡ አስተያየቶች የመስተንግዶውን ፍላጎት አድርገውታል፡፡ ለሱፕር ስፖርት በሰጡት አስተያየት አፍሪካ ዋንጫ ለማዘጋጀት ያለንን ፍላጎት መላው ኢትዮጵያዊያንና እና የአፍሪካ አገራት ከደገፉት ይሳካል ያሉት የኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌደሬሽኑ ፕሬዝዳንት አቶ ጁነዲን ባሻ  ናቸው፡፡
‹‹የአፍሪካ ዋንጫን ማዘጋጀት፤ በአህጉሪቱ እግር ኳስ ያለንበትን ከፍታ ለማሳየት እድል ይፈጥራል›› ብሎ የተናገረው ደግሞ ኤልሻዳይ ነጋሽ የተባለው ታዋቂ ጋዜጠኛ ነው፡፡ አዲስ አበባ በአፍሪካ የባቡር ሜትሮ ኔትዎርክ ካላቸው ጥቂት ከተሞች አንዷ መሆኗን፤ በመሰረተ ልማት እየተጠናከረች መምጣቷን ለሱፕር ስፖርት የገለፀው ኤልሻዳይ  ፤ የፓን አፍሪካኒዝም መዲና በሆነች ከተማ ውድድሩ መዘጋጀቱ ተገቢ ነው በማለት ድጋፉን ገልጿል፡፡ ‹‹የእግር ኳስ ፌደሬሽኑ ለውድድሩ አዘጋጅነት ፍላጎት ማሳየቱን ስሰማ በጣም ጉጉት ፈጥሮብኛል፡፡ ለእኛ ተጨዋቾች አፍሪካ ዋንጫን በሜዳችን በደጋፊችን ፊት መጫወት ከፍተኛ ሞራል እና መነቃቃትን የሚፈጥር ይሆናል፡፡ ሁሉም ኢትዮጵያውያን ፌደሬሽኑን እና መንግስትን በሙሉ አቅም መደገፍ አለባቸው፡፡  በዚህም አፍሪካ ዋንጫ የማዘጋጀት ህልምን ማሳካት ይቻላል፡፡›› በማለት ለሱፕር ስፖርት የድጋፍ አስተያየት ያቀበለው የብሄራዊ ቡድኑ ተጨዋች አበባው ቡጣቆ ነው፡፡ የብሄራዊ ቡድኑ ወሳኝ የአማካይ መስመር ተሰላፊ የሆነው ሽመልስ በቀለ በበኩሉ ‹‹አስደሳች  እና ታላቅ ዜና ነው፡፡ ኢትዮጵያ የአፍሪካ ዋንጫ አዘጋጅነት እንደሚሳካላት ተስፋ አደርጋለሁ፡፡   አዘጋጅ ሆነች የሚለውን ዜና በጉጉት እጠብቃለሁ፡፡›› በማለት ተናግሯል፡፡
ከ29 የአፍሪካ ዋንጫዎች በአስሩ ላይ መሳተፍ የቻለችው ኢትዮጵያ ለሶስት ጊዜያት የአፍሪካ ዋንጫ አዘጋጅ ነበረች፡፡ በ1962 ውድድሩን በማዘጋጀት ሻምፒዮን ስትሆን እንዲሁም በሌሎች ባዘጋጀቻቸው ሁለት የአፍሪካ ዋንጫዎች በ1968 እኤአ ላይ አራተኛ ደረጃ እና በ1976  እኤአ ደግሞ ከመጀመርያው ዙር ከውድድሩ ተሰናብታለች፡፡ ከኢትዮጵያ ሌላ የውድድሩን አዘጋጅነት ለመረከብ ፍላጎታቸውን የገለፁት አገራት አምስት ደርሰዋል፡፡ የመጀመርያዋ ኬንያ ስትሆን የአፍሪካ ዋንጫውን ከጐረቤቶቿ ታንዛንያ፣ ኡጋንዳ እና ሩዋንዳ ጋር በጣምራ የማዘጋጀት ጥያቄ አቀርባለሁ እያለች ነው፡፡ የምእራብ አፍሪካዋ ጋና እና የደቡብ አፍሪካዋ ዛምቢያም አዘጋጅነቱን እንደሚፈልጉ ሲያስታውቁ በመጨረሻም ለመስተንግዶ ፍላጎቷን እያሳየች የመጣችው አልጄርያ ናት፡፡ 16 ብሄራዊ ቡድኖች የሚሳተፉበትን የአፍሪካ ዋንጫ ለማዘጋጀት ዓለም አቀፍ ደረጃን የሚያሟሉ ስታድዬሞች፤ የሆቴል እና የትራንስፖርት መሰረተልማቶች እጅግ ወሳኝ ሲሆኑ እስከ 55 ሚሊዮን ዶላር በጀት እንደሚያስፈልግም ይገመታል፡፡

       በሳምንቱ መግቢያ ላይ በሮም ከተማ በሚገኘው ስታድዮ ኦሎምፒኮ በተዘጋጀው የዓለም ሃይማኖቶች ሁሉን አቀፍ የሰላም ግጥሚያ ላይ የዋልያዎቹ የቀድሞ ዋና አምበል ደጉ ደበበ ተሳተፈ፡፡ የእግር ኳስ ግጥሚያውን በክብር እንግድነት የታደሙት የቫቲካኑ ጳጳስ ፍራንሲስ ሲሆኑ፤ የሰው ልጆች በጭራሽ ሰይፍ የማይማዘዙበት ዘመን እንዲመጣ ሃይማኖት እና ስፖርት ከፍተኛ አስተዋፅኦ አላቸው ሲሉ ተናግረዋል፡፡
በዓለም እግር ኳስ የታዩ ከ50 በላይ የአሁን ዘመንና የቀድሞ እግር ኳስ ተጨዋቾች በሰላም ግጥሚያው ተሳታፊ ነበሩ፡፡ ለሁለቱ ቡድኖች ተሰላፊዎችን የመረጡት አዲሱ የአርጀንቲና ብሄራዊ ቡድን አሰልጣኝ ጌራርዶ ታታ ማርቲኖ እና የአርሰናሉ አሰልጣኝ አርሰን ቬንገር ናቸው፡፡ በሁለቱ ቡድን የተመረጡ ተጨዋቾች በግጥሚያው የሁለት ግብረሰናይ ተቋማትን የሚወክሉ ማልያዎችን ለብሰው ተሳትፈዋል፡፡ በሃቪዬር ዛኔቲ አምበልነት የሚመራው ፑፒስ እና  በጂያንሉጂ ቡፎን የሚመራው ስኮላስ ናቸው፡፡
በጨዋታው ተሳታፊ ከሆኑት የጊዜያችን ምርጥ ተጨዋቾች መካከል ሊዮኔል ሜሲ፤ ኤቶና ፒርሎ እንዲሁም ከአንጋፋዎች ዲያጐ ማራዶና፣ ዴልፒዬሮና ሮበርቶ ባጂዮ ይገኙበታል፡፡
 የዓለም ህዝቦችን አንድነት ለማጠናከር ጉልህ ሚና እንደሚኖርበት የታመነበት የሰላም ግጥሚያው በመላው ዓለም ሰላምን ለማስፋፋት ቅስቀሳ የተደረገበት ሲሆን በከፋ አደጋ ላይ ለሚገኙ የዓለም ህፃናት ድጋፍ የሚሆን ገቢም ተሰባስቦበታል፡፡  የሰላም ግጥሚያውን ስፖንሰር ካደረጉት መካከል ዓለም አቀፉ እግር ኳስ ማህበር ፊፋ፤ የዓለም ምግብ ፕሮግራም ፋኦ፤ የመኪና አምራቹ ኩባንያ ፊያት እና ሌሎች ትልልቅ ዓለም አቀፍ ኩባንያዎች ይጠቀሳሉ፡ በመላው ዓለም በአምስት አህጉራት በቴሌቭዥን የቀጥታ ስርጭት የነበረው ዝግጅቱ በጣሊያን፤ በኦስትርያ፤ በፈረንሳይ እና በጀርመን ልዩ  ትኩረት እንዳገኘም ታውቋል፡፡
በዓለም ሰላም እንዲሰፍን ለመቀስቀስ የተዘጋጀውን የእግር ኳስ ልዩ  ግጥሚያ በማስተባበር በቦነስ አይረስ የሚገኘውን ፑፒ ፋውንዴሽን መስራች የቀድሞው አርጀንቲናዊ ተጨዋች ሃቪዬር ዛኔቲ ጉልህ አስተዋፅኦ አበርክቷል፡፡
  ሃቪዬር ዛኔቲ  በአርጀንቲና ብሄራዊ ቡድን አምበልነት ያገለገለ፤ በሚላን ከተማው ክለብ ኢንተር ሚላን ለ19 ዓመታት የተጫወተ እና አሁን የክለቡ ምክትል ፕሬዝዳንት ሆኖ እየሰራ ነው፡፡

       በኢትዮጵያ እናቶች በአማካይ በሕይወት ዘመናቸው የሚወልዱት ልጅ መጠን በ2005 /5.4/ በ2011 /4.8/ (DHS)› ሲሆን በ2015 ይህን ቁጥር ወደ /4.4/ ዝቅ የማድረግ እቅድ ተይዞአል ፡፡ በዚህ ዙሪያ በተለይም ቋሚና የረዥም ጊዜን የመከላከያ ዘዴዎች ጠቀሜታን እና የጎንዮሽ ጉዳታቸውን ዶ/ር ነጋ ተስፋው የጽንስና ማህጸን ሕክምና እስፔሻሊስት አብራርተዋል፡፡ ዶ/ር ነጋ  በአሁኑ ወቅት በማሪስቶፕስ ኢንተርናሽናል ኢትዮጵያ የጥራትና የህክምና አገልግሎት ዳይሬክተር ሆነው ይሰራሉ፡፡
ጥ/ የረዥም ጊዜ የእርግዝና መከላከያዎች ሲባል ምን ማለት ነው?
መ/ የእርግዝና መከላከያዎች የተለያዩ ናቸው፡፡ በተወሰነ የጊዜ እርቀት ወይንም በየእለቱ ከሚወሰዱት በኪኒን መልክ እና በመርፌ ከተዘጋጁት ውጪ ለረዥም ጊዜ እንዲሁም በቋሚነት እርግዝናን ለመከላከል የሚያስችሉ ዘዴዎች አሉ፡፡ የረጅም ጊዜ የሚባሉት በማህጸን ውስጥ እስከ 12/ አመት ድረስ መቀመጥ የሚችል (IUD) ወይንም ሉፕ እና በክንድ ቆዳ ስር እስከ አምስት አመት ድረስ በመቆየት ያልተፈለገ እርግዝናን መከላከል የሚችያስችል የህክምና ዘዴ ነው፡፡ እነዚህ ሁለቱም መከላከያዎች 99 % ያህል አስተማማኝ የእርግዝና መከላከያዎች ሲሆኑ ሕክምናው የሚሰጠውም ለሴቶች ነው፡፡
ጥ/ (IUD)  ሉፕ የተባለው የረዥም ጊዜ የእርግዝና መከላከያ በማህጸን ውስጥ ለ12/አመት ያህል ሲቆይ ችግር አያመጣም?
መ/ (IUD)  ሉፕ ለረጅም ጊዜ አገልግሎት ላይ የሚውል በመሆኑ እንደመርፌ ወይንም እንክብል በየጊዜው ውሰዱኝ የማይል እና ጊዜውን በትክክል ባለመጠበቅ ምክንያት ችግር የሚያስከትል አይደለም፡፡ ምናልባትም ሕክምናው በተሰጠ ለመጀመሪያዎቹ የሶስት ወራት የወር አበባ መዛባት ሊያስከትል ቢችልም ይህም ጊዜ ሳይፈጅ የሚስተካከል በመሆኑ ምንም አያሳስብም፡፡ በማህጸን ውስጥ ለረጅም ጊዜ ወይንም እስከ 12/አመት ድረስ በመቆየቱም የመመረዝ ወይንም የመቆሸሽ እድል የማይገጥመው ሲሆን በየመሀሉ ማውጣት የሚያስፈልገው አይደለም፡፡ ተጠቃሚዋ በፈለገችው ጊዜ እንዲወጣ ከማድረግ በስተቀር እስከ12/ አመት ድረስ ካለምንም ችግር ሊቆይ የሚችል አስተማማኝ የመከላከያ ዘዴ ነው፡፡ ..ህ.... ሉፕ ቀላል የሆነ የመከላከያ ዘዴ ሲሆን ለተጠቃሚዎችም ምቹ የሆነ እና ከባድ የጤና ችግር የማያስከትል ተስማሚ የሆነ የህክምና ዘዴ ነው፡፡
ጥ/ (IUD)   ሉፕ የተባለው የእርግዝና መከላከያ አንዳንዴ እርግዝናን ሳይከላከል ከልጅ ጋር አብሮ ይወለዳል?
መ/ በመጀመሪያ ደረጃ የረጅም ጊዜ የእርግዝና መከላያ (IUD)   ሉፕ 99 % ያህል እርግዝናን የመከላከል አቅም ያለው ስለሆነ እርግዝናው ይከሰታል ተብሎ አይጠበቅም፡፡ አንዳንድ ጊዜ ግን ከኑሮ ሁኔታ ወይንም የግብረስጋ ግንኙነቱ ባህርይ በሚፈጥረው ተገቢ ያልሆነ እንቅስቃሴ እርግዝናው ቢከሰት እርግዝናው ጊዜው ሳይገፋ ክሩ የሚታይ ከሆነ ሉፑን በቀላሉ ስቦ ማውጣት ይቻላል፡፡ምናልባት ትኩሳት ወይንም የደም መፍሰስ ቢያጋጥም ግን ወደሐኪም በመሔድ መታየት ያስፈልጋል፡፡  ሳይታወቅ እርግዝናው የገፋ እና (IUD)    ሉፑም ክሩ የማይታይ ከሆነ ግን ከልጁ ጋር አብሮ ቢወለድ ምንም ጉዳት አያስከትልም፡፡ በአጠቃላይ ግን (IUD)    ሉፕ በማህጸን ውስጥ በሚቀመጥበት ጊዜ የሚሰጥ የህክምና ባለሙያዎች ምክር ስለሚኖር ያንን በትክክል ተግባራዊ ማድረግ ከተጠቃሚዎች ይጠበቃል፡፡
ጥ/ ቋሚ የእርግዝና መከላከያዎች ምን አይነት ናቸው?
መ/ ቋሚ የሚባለው የእርግዝና መከላከያ  በቀዶ ሕክምና ለሴቷም ሆነ ለወንዱ የሚሰጥ የመከላከያ ዘዴ ነው፡፡  ቋሚ የሚባለው የእርግዝና መከላከያ ዘዴ በተለያየ የጋብቻ ሁኔታ ፣የስራ መስክ ፣የእድሜ ክልልና የኑሮ ሁኔታ ላይ የሚገኙ ተጨማሪ ልጅ ለመውለድ የማይፈልጉ ሴቶችና ወንዶች የሚመርጡት ዘመናዊ ዘዴ ነው፡፡ ይህ የቤተሰብ እቅድ ዘዴ ለወንዶችም ሆነ ለሴቶች በቀላል የቀዶ ሕክምና የሚሰጥ ፣ ለሕይወት ዘመን በቋሚነት እርግዝናን የሚከላከል አስተማማኝና በጤና ላይ ምንም ጉዳት የማያስከትል ነው፡፡ ለሴቷ የሚደረገው ቋሚ የእርግዝና መከላከያ ዘዴ የዘር መተላለፊያውን ቱቦ በመቋጠር ሲሆን የወንዱ ቋሚ የእርግዝና መከላከያ ዘዴ የወንዱ የዘር ፈሳሽ መተላለፊያን በመቋጠር እርግዝናን በቋሚነት መከላከል የሚያስችል ዘዴ ነው፡፡
ጥ/ ከቀዶ ሕክምናው በሁዋላ ተጠቃሚዎች ምን ጥንቃቄ ሊያደርጉ ይገባል?
መ/ ቀዶ ሕክምናው በጣም ቀላል በመሆኑ ምክንያት ከጥቂት ቆይታ በሁዋላ አገልግሎቱን ያገኙ ሁሉ ወደቤታቸው ይሄዳሉ፡፡ በተለይም ሴቶች ከሆኑ ለሁለት ቀናት ያህል በቤታቸው ከባድ ስራን ከመስራት እንዲቆጠቡ እና በቂ እረፍት እንዲያደርጉ ይመከራል፡፡ ሴቶች ለአንድ ሳምንት ወይንም ቁስሉ እስኪድን ድረስ ከግብረስጋ ግንኙነት መታቀብ ይኖርባቸዋል፡፡ ወንዶችን በሚመለከት ከቀዶ ሕክምናው በሁዋላ እንደሴቶቹ ለሁለት ቀናት ያህል በቂ እረፍት ማድረግ የሚገባቸው ሲሆን የግብረስጋ ግንኙነትን በሚመለከት ግን ከቀዶ ሕክምናው በሁዋላ ለሶስት ወራት ያህል የማስረገዝ እድል ስለሚኖር  መታ ቀብ፣ ሚስትየዋ ሌላ ዘዴ እንድትጠቀም ማድረግ ወይንም ኮንዶም ሁልጊዜና በአግባቡ መጠቀም ያስፈልጋል፡፡
ጥ/    አገልግሎቱን ያገኙ ሴቶችም ሆኑ ወንዶች ተመልሰው ወደጤና ድርጅት መሄድ ያስፈልጋቸዋልን?  
ሴቶች
* ከፍተኛ ትኩሳት፣
* በታችኛው የሆድ ክፍል ከባድ ሕመም፣
* የቁስሉ እብጠት ቅላትና መመርቀዝ.. መምገልና መድማት..  የሚያዩ ከሆነ በፍጥነት ወደሕክምናው ተቋም መሄድ ያስፈልጋቸዋል፡፡
ወንዶች
* ቀዶ ሕክምናውን ካደረጉ ከጥቂት ቀናት በሁዋላ በቀዶ ሕክምናው ቦታ ላይ እብጠት ከተፈጠረ፣
* ቁስሉ ከመድረቅ ይልቅ የማመርቀዝ ፣የመድማት ወይም የመምገል ምልክት ካሳየ ወደ ሕክምና ተቋም መሔድ ይጠበቅባቸዋል፡፡
ጥ/ ቋሚ የእርግዝና መከላከያ ምን ያህል ተጠቃሚ አለው?
መ/በአለም አቀፍ ደረጃ ሁለቱም ማለትም ወንዶችም ይሁኑ ሴቶች በከፍተኛ ሁኔታ ተጠቃሚ  ሆነው ይታያሉ፡፡ በአገራችን ግን እስከአሁን በአለው ልምድ ተጠቃሚው በአብዛኛው መርፌውን የሚመርጥ የነበረ ቢሆንም አሁን ግንቋሚ የእርግዝና መከላከያ ዘዴው ከውሳኔ በደረሱ ሰዎች ዘንድ በስፋት እየተለመደ እና በስራ ላይ እየዋለ ያለ ነው፡፡ ይህ ያልተፈለገ የእርግዝና መከላከያ ዘዴ ሁለቱ ጥንዶች ተስማምተው ወይንም በግልም ቢሆን በእርግጠኝነት በቂ ልጅ ስለአለኝ ወደፊት ልጅ መውለድ አልፈልግም ከሚል ውሳኔ ላይ እስከደረሱ ድረስ ደስተኛ የሆነ ሕይወትን ለመምራት የሚያስችል የእርግዝና መከላከያ ዘዴ ነው፡፡
ጥ/ ቋሚ የእርግዝና መከላከያ ጉዳት አለውን?
 መ/ በሕክምናው ዘዴ የሚደርስ ምንም አይነት ጉዳት የለም፡፡ ወንድም ሆነ ሴት የቋሚ የእርግዝና መከላከያ እንዲወስዱ በሚወስኑበት ጊዜ ግን መጠንቀቅ ያለባቸው ነገር አለ፡፡
* በጊዜያዊ የኑሮ ሁኔታዎች ተገፋፍቶ፣
* በትዳር ጉዋደኛ አሳማኝነት ወይንም ግፊት ብቻ ተመርቶ፣
* ስሜትን ወይንም የእራስን ፍላጎት በደንብ ሳያዳምጡ፣
* ከሚመለከተው ቅርብ ከሆነው የትዳር ጉዋደኛ ጋር በትክክል ተወያይተው ሳይወስኑ፣
* በአጠቃላይም ሁኔታዎችን በትክክል ሳያመዛዝኑ ...ወዘተ
በዚህ መልክ እርምጃ በአካልዎ ላይ ከወሰዱ በእርግጥ ውጤቱ የሚጸጽት ሊሆን ይችላል፡፡ ከዚህ በተረፈ ግን በሁኔታው አምነው እርምጃ ከወሰዱ ሕክምናው ቀላል እና ከማንኛውም አይነት የኑሮ ሁኔታ ወይንም ከፍቅር ግንኙነት የማያግድ መሆኑን ባለሙያዎችም ሆኑ ተጠቃሚዎች የሚመሰክሩት ነው፡፡ ቋሚና የረዥም ጊዜ የእርግዝና መከላከያዎች አስተማማኝ እና ለተጠ ቃሚዎች ተስማሚ በመሆናቸው ህብረተሰቡ ይህንን ተረድቶ አስፈላጊ በሆነ ጊዜ  እንዲጠ ቀምበት ይመከራል፡፡

*    ጋዛን መልሶ ለመገንባት 6 ቢሊዮን ዶላር ያስፈልጋል
*    እስራኤል ለጦርነቱ 2. 3 ቢሊዮን ዶላር አውጥታለች

ለሰባት ሳምንታት ያህል ከወደ እስራኤል ቀን ከሌት ሲሰነዘርባት በቆየው አሰቃቂ ድብደባ አሳር መከራዋን ስታይ የቆየችው የፍልስጤሟ ጋዛ፣ ከቀናት በፊት በተደረሰው የተኩስ አቁም ስምምነት ለጥቂት ጊዜም ቢሆን እፎይ ብትልም፣ ድብደባው ያደረሰባት ጥፋት ግን እጅጉን የከፋና በቀላሉ የሚሽር አይደለም፡
በሁለቱ ሃይሎች መካከል የተፈጠረው ግጭት ለ70 እስራኤላውያን ሞት ምክንያት መሆኑ እንዳለ ሆኖ፣ ግጭቱ እጅግ የከፋ ሰብዓዊና ኢኮኖሚያዊ ጥፋት ያስከተለው ግን፣ በፍልስቴም ላይ መሆኑን የኣለማችን መገናኛ ብዙሃን እየመሰከሩ ይገኛሉ፡፡
ግጭቱ ለህልፈተ ህይወት ከዳረጋቸው 2ሺህ በላይ ፍልስጤማውያንን መካከል አብዛኞቹ ጨቅላ ህጻናት ሰለመሆናቸው የዘገበው ሲኤንኤን፣ ለሳምንታት ስትደበደብ የቆየችው ጋዛ እንዳታገግም ሆና መፈራረሷንና የደረሰባት ኢኮኖሚያዊ ቀውስም እጅግ የከፋ እንደሆነ ገልጧል፡፡
በእስራኤል ጥቃት የፈራረሰችዋን ጋዛ መልሶ ለመገንባት ከፍተኛ ገንዘብ እንደሚጠይቅ የጠቆመው ሲኤንኤን፣ መልሶ ግንባታውን በተገቢው መንገድ ለማከናወን እስከ 6 ቢሊዮን ዶላር የሚደርስ የገንዘብ  እንደሚያስፈልግ ገልጧል፡፡የተባበሩት መንግስታት ድርጅትና አጋሮቹ በጋዛ ለሚከናወኑ የሰብዓዊ መልሶ ማቋቋም ስራዎች ተጨማሪ 367 ሚሊዮን ዶላር እንደሚያስፈልግና፣ ከዚህ ገንዘብ ውስጥም ከግማሽ በላይ የሚሆነው የጥቃቱ ሰለባ የሆኑ ከ500ሺህ በላይ የጋዛ ነዋሪዎችን የምግብ ዋስትና ለማረጋገጥ፤ የተቀረው ገንዘብም ለቤቶች ግንባታ፣ ለውሃና ንጽህናና ለትምህርት ተቋማት ግንባታ እንደሚውል ገልጠዋል፡፡
ኦክስፋም በበኩሉ በጋዛ ነዋሪዎች ላይ የደረሰው የመሰረተ ልማት አውታሮች ውድመት፣ በአለማችን ባለፉት 20 አመታት ከተከሰቱ መሰል ውድመቶች ሁሉ ባደረሰው ቀውስ ከፍተኛነት ወደር እንደማይገኝለት ገልጧል፡፡ ከ15 በላይ ሆስፒታሎች እና በጋዛ ብቸኛው የነበረው የሃይል ማመንጫ፣ ከእስራኤል በደረሰባቸው የድብደባ ጥቃት ሙሉ ለሙሉ መፈራረሳቸውንም ተናግሯል፡፡
በጋዛ እስካለፈው ነሃሴ 3 ቀን ድረስ ከ10    ሺህ 600 በላይ መኖሪያ ቤቶች መውደማቸውን የጠቆመው የተባበሩት መንግስታት ድርጅት የልማት ፕሮግራም፣ የፈራረሱትን ቤቶች መልሶ የመገንባቱ ስራ እጅግ ፈታኝ እንደሚሆንና ምናልባትም አራት አመታትን ያህል ጊዜ ሊፈጅ እንደሚችል አስታውቋል፡፡
የእስራኤል የታክስ ባለስልጣን በበኩሉ፣ ከሃማስ በተሰነዘሩ ጥቃቶች የወደሙ የአገሪቱ ቤቶችን ቁጥር በተመለከተ ተጨባጭ መረጃ ባይኖርም፣ የመሰረተ ልማት አውታሮችን መልሶ ለመገንባት ግን 11 ሚሊዮን ዶላር ያህል ወጪ እንደሚጠይቅ አስታውቋል፡፡
የእስራኤል መንግስት የንብረት ውድመት ለደረሰባቸው ዜጎቹ ማካካሻ ገንዘብ እየሰጠ እንደሚገኝ የጠቆመው የሲኤንኤን ዘገባ፣ ከፍተኛ የመሰረተ ልማት አውታሮች ውድመት በደረሰባት የሰሜን እስራኤሏ ከተማ የአሽዶድ ነዋሪዎችን ጨምሮ፣ 3ሺህ 700 ያህል የአገሪቱ ዜጎች ለመንግስት የማካካሻ ገንዘብ ጥያቄ ማመልከቻ ማቅረባቸውንና ከግማሽ በላይ የሚሆኑትም ለመኖሪያ ቤት ውድመት ያመለከቱ መሆናቸውን ገልጧል፡፡
ግጭቱ በእስራኤል የቱሪዝም ገቢ ላይ ከፍተኛ ተጽዕኖ መፍጠሩን፣ ምርታማነት ላይ ቅናሽ እንዲፈጠር ማድረጉንና ይህም የሆነው በርካታ የአገሪቱ ሰራተኞች የሮኬት ጥቃትን በመፍራት ስራ አቋርጠው በመኖሪያ ቤቶቻቸው በመደበቃቸው እንደሆነም አስረድቷል፡፡
እስራኤል ለሰባት ሳምንታት ያህል በጋዛ ላይ በሰነዘረችው ጥቃት ያወጣችውን አጠቃላይ ወታደራዊ ወጪ በተመለከተ ይፋዊ መረጃ ባትሰጥም፣ የአገሪቱ መገናኛ ብዙሃን ግን ወጪው እስከ 2 ነጥብ 3 ቢሊዮን ዶላር ይደርሳል እያሉ ነው፡፡

በአመት 3.6 ሚ. ዜጎች በሙስና ሰበብ ለህልፈተ ህይወት ይዳረጋሉ

በድሃ ሃገራት በአመት 1 ትሪሊዮን ዶላር የሚገመት ገንዘብ በሙስና ተመዝብሮ ከአገር እንደሚወጣና በአንድ አመት ጊዜ ውስጥም በሚሊዮኖች የሚቆጠሩ ዜጎች በሙስና ሰበብ ለህልፈተ ህይወት እንደሚዳረጉ አንታይፖቨርቲ ኦርጋናይዜሽን ዋን የተባለ ተቋም ያወጣውን ሪፖርት ጠቅሶ ቢቢሲ ዘገበ፡፡
በድሀ አገራት የሚታየውን የከፋ ድህነት ለመቅረፍ ባለፉት ሁለት አስርት አመታት ሲደረጉ የነበሩ አበረታች ጥረቶች በሙስና ሳቢያ እየተደናቀፉ እንደሚገኙ የጠቆመው ዘገባው፣ በአገራቱ በከፍተኛ ሁኔታ በመስፋፋት ላይ በሚገኘው ሙስና ሳቢያ በየአመቱ ከፍተኛ መጠን ያለው ገንዘብ ተመዝብሮ እንደሚወጣና ዜጎችም ለህልፈተ ህይወት እየተዳረጉ እንደሚገኙ ገልጧል፡፡
ሙስና በደሃ የዓለማችን አገራት ከበሽታዎችና ከተፈጥሮ አደጋዎች በበለጠ ሁኔታ የኢኮኖሚና የሰብዓዊ ቀውስ እየፈጠረ እንደሚገኝ የገለጸው የተቋሙ ሪፖርት፣ ድርጊቱ የግል ኢንቨስትመንትን የሚያደናቅፍ፣ የኢኮኖሚ እድገትን የሚገታና የንግድ እንቅስቃሴ ወጪዎችን ያለአግባብ የሚያንር ከመሆኑ በተጨማሪ ፖሌካዊ አለመረጋጋት እንዲፈጠር ያደርጋል ብሏል፡፡በማደግ ላይ ያሉ አገራት የገንዘብ ሃብት በሙስና እየተመዘበረ ከአገር እንዲወጣ መደረጉ፣ የአገራቱ መንግስታት ለጤና እንክብካቤ፣ ለምግብ ዋስትናና ለሌሎች መሰረታዊ መሰረተ ልማቶች ማስፋፊያ በቂ በጀት እንዳይመድቡ እንቅፋት ስለሚፈጥር፣ በአገራቱ በየአመቱ በሚሊዮኖች የሚቆጠሩ ዜጎች፣ በተለይ ደግሞ በርካታ ቁጥር ያላቸው ህጻናት ለህልፈተ ህይወት እንደሚዳረጉ ሪፖርቱ ገልጧል፡፡ከሰሃራ በታች በሚገኙ የአፍሪካ አገራት ሙስናን ማጥፋት ቢቻል፣ በየአመቱ 10 ሚሊዮን ተጨማሪ ህጻናትን የትምህርት እድል ተጠቃሚ ማድረግ፣ ለተጨማሪ 500 ሺህ የአንደኛ ደረጃ መምህራን ደመወዝ መክፈል እንዲሁም ከ11 ሚሊዮን በላይ ለሚሆኑ ሰዎችም የጸረ ኤች ኤቪ ኤድስ መድሃኒት በአግባቡ ማዳረስ ይቻል እንደነበርም በሪፖርቱ መገለጹንም ዘገባው ጨምሮ ገልጧል፡፡