Administrator

Administrator

ነገ የሦስት ወር ንቅናቄውን በአዲስ አበባ ይጀምራል

      ከመድረክ ጋር ያለውን ጥምረት አቋርጦ ከሌሎች ፓርቲዎች ጋር የውህደት ድርድር የጀመረው አንድነት ለፍትህና ለዲሞክራሲ ፓርቲ፤በመጪው ዓመት ምርጫ የሚሳተፈው የምርጫው አስፈፃሚ አካላት ነፃና ገለልተኛ መሆናቸው ከተረጋገጠ ብቻ እንደሆነ  ሊቀመንበሩ ኢ/ር ግዛቸው ሽፈራው ገለፁ፡፡
በ97 ምርጫ ቅንጅት የነበረውን ጥንካሬ ፓርቲያቸው መድገም እንደሚፈልግ የገለፁት ኢ/ር ግዛቸው፤ ህዝቡ ብሶት ላይ ስለሆነ በምርጫው ተቃዋሚዎች በቀላሉ ሊያሸንፉ እንደሚችሉ ተናግረዋል፡፡ ፓርቲያቸው ወደ ምርጫው የሚገባው ግን ለምርጫው ነፃና ፍትሃዊ መሆን አስፈላጊ የሚባሉት ገለልተኛ የምርጫ ቦርድ፣ ሚዲያ እና የፍትህ ተቋማት መኖራቸውን ካረጋገጠ በኋላ እንደሆነ ተናግረዋል፡፡ “ይህ ጥያቄያችን ከተመለሰ በምርጫው በእርግጠኝነት እናሸንፋለን” ብለዋል የፓርቲው መሪ፡፡
ፓርቲያቸው ከመድረክ ጋር ስላለው ግንኙነት የተጠየቁት ኢ/ር ግዛቸው፤ አንድነት ከቢሮ እና ከመግለጫ ፖለቲካ ተላቆ ትግሉን ወደ ህዝብ ለማውረድ  ያደረገው እንቅስቃሴ የመድረክ አመራሮችን እንዳስኮረፈና እገዳው እንደተላለፈ ጠቅሰው “እገዳው ትክክል አይደለም፤ አንሱትና ባቀረብነው የውህደት ጥያቄ መሰረት አብረን እንስራ ብለናቸዋል” ብለዋል፡፡
“መድረክ ከአንድነት የተሻለ ጥንካሬ እንደሌለው ገምግመናል” ያሉት ሊቀመንበሩ፤ ውህደቱን አንፈልግም ቢሉም እንኳን በሚያግባቡን ጉዳዮች ላይ በቅንነት አብረን ልንሰራ እንደምንችል ነግረናቸዋል ብለዋል፡፡
ከእዚህ በኋላ አንድነት በቀጥታ ውህደት ከመፈፀም ውጪ ከየትኛውም ፓርቲ ጋር ግንባርና ቅንጅት የመፍጠር ፍላጎት እንደሌለውም ኢ/ር ግዛቸው ጨምረው ገልፀዋል፡፡
ፓርቲው በነገው እለት “የሚሊዮኖች ድምፅ ለነፃነት” ሁለተኛ ዙር ንቅናቄ በአዲስ አበባ የሚጀምር ሲሆን  አጀንዳውም መሬት የግል እንዲሆን የሚጠይቅ ነው ተብሏል፡፡ ለ3 ወር ይዘልቃል የተባለውን ይሄን ንቅናቄ በተመለከተ የተጠየቁት ኢ/ር ግዛቸው፤“በአንድነት ፕሮግራም ውስጥ ከመንግሥት ይዞታና ከአንዳንድ ተቋማት ይዞታ በስተቀር መሬት የግል መሆን አለበት በሚል በግልፅ አስቀምጠናል፡፡ ይህን መነሻ አድርገን በመሬት ጉዳይ ላይ ህዝብ ተወያይቶ የራሱን አቋም የሚይዝበት ትልቅ ንቅናቄ አዘጋጅተናል” ሲሉ አስረድተዋል፡፡
 አሁን ያለው የመሬት ፖሊሲ ለኑሮ ውድነቱ መባባስ አስተዋፅኦ አበርክቷል ያሉት ኢ/ር ግዛቸው፤ “የኑሮ ውድነቱ ካለን የመሬት ሃብት ተጠቃሚ ያለመሆናችን ውጤት ስለሆነ፣ ጥያቄያችን የኑሮ ውድነት አጀንዳንም በበቂ ሁኔታ የያዘ ነው” ብለዋል፡፡ መንግስት በበኩሉ፤ መሬት የህዝብና የመንግስት ነው የሚል ፖሊሲ እንደሚያራምድ ይታወቃል፡፡
(ከአንድነት ፓርቲ ሊቀመንበሩ ኢ/ር ግዛቸው ሽፈራው ጋር የተደረገው ቃለምልልስ ሙሉ ቃል በገፅ 5 ላይ ያገኙታል፡፡)


          የ38 አመቱ ኢትዮጵያዊ ዶክተር ፍሰሃ ኡንዱቼ በካናዳ የመሰረተ ልማትና የትራንስፖርት ሚኒስቴር የማኒቶባ ግዛት የአየር ንብረትና የጎርፍ አደጋ ትንበያ ዳይሬክተር ሆነው መመረጣቸውን ዊኒፒንግ ፍሪ ፕሬስ ዘገበ፡፡
የካናዳ የመሰረተ ልማትና የትራንስፖርት ሚኒስትር ስቲቭ አሽተን ዶክተሩን ለመገናኛ ብዙሃን ለማስተዋወቅ በተዘጋጀ ስነስርዓት ላይ ተገኝተው እንደተናገሩት፣ ከተለያዩ አገራት የተውጣጡ በርካታ ባለሙያዎች የተሳተፉበትን ከፍተኛ ውድድር በማሸነፍ ለማኒቶባ ግዛትየአየር ንብረትና የጎርፍ አደጋ ዳይሬክተር ለመሆን የተመረጡት ዶክተር ፍሰሃ፣ ላለፉት 15 አመታት በሃይድሮሎጂና ከጎርፍ አደጋ ጋር በተያያዙ ጉዳዮች በአሜሪካና በተለያዩ የአውሮፓ አገራት የካበተ የስራ ልምድ አላቸው፡፡
ላለፉት አምስት አመታት የግዛቷ የውሃ ቁጥጥር ስርዓቶች ዕቅድ ከፍተኛ መሃንዲስ ሆነው ያገለገሉት ዶክተር ፍሰሃ፣ ከዚያ ቀደምም ኤኢኮም በተባለ አለማቀፍ የምህንድስና አገልግሎቶች ኩባንያ ውስጥ የውሃ ሃብቶች መሃንዲስ ሆነው ማገልገላቸው ተነግሯል፡፡ ኒዘርላንድ ውስጥ ከሚገኘው ኢንተርናሽናል ሃይድሮሊክ ኢንጂነሪንግ ኢንስቲቲዩት በሲቪል ምህንድስና የሁለተኛ ዲግሪያቸውን የተቀበሉት ዶክትር ፍሰሃ፣ በኖርዌጂያን ዩኒቨርሲቲ ኦፍ ሳይንስ ኤንድ ቴክኖሎጂ ሌሎች የምርምር ጥናቶችን እንደሰሩ ተጠቁሟል፡፡
ከማኒቶባ ዩኒቨርሲቲ በውሃ ሃብቶች የዶክትሬት ዲግሪያቸውን ከተቀበሉ በኋላም፣ በተለያዩ ተቋማት ውስጥ ከጎርፍ አደጋ ትንበያና ከአደጋ ቁጥጥር ጋር በተያያዙ ጉዳዮች በውሃ ሃብቶች መሃንዲስነትና በመምህርነት አገልግለዋል፡፡በወቅቱ ከጋዜጠኞች ጥያቄ የቀረበላቸው ዶክትር ፍሰሃ፣ በውሃው ዘርፍ የጀመሩትን ጥናት አጠናክረው ለመቀጠል የሚያስችሏቸውን የጎርፍ አደጋዎች የሚበዙባቸው አካባቢዎችና በጎርፍ አደጋ ትንበያ ላይ ልዩ ትኩረት አድርገው የሚሰሩ ዩኒቨርሲቲዎች ሲያጠኑ እንደቆዩና ማኒቶባ ግዛት ለዚህ ተመራጭ መሆኗን በማረጋገጥ ወደዚያው ለመሄድ መወሰናቸውን ተናግረዋል፡፡
ዶክተር ፍሰሃ ባለትዳርና የሁለት ልጆች አባት ናቸው፡፡




           አምስቱ የአድዋ ተጓዦች ከአዲስ አበባ 260 ኪ.ሜ አካባቢ ወለቲ በተባለች ትንሽ ከተማ የበእምነት ደገፉ እናት የነገሯቸውን አሳዛኝ ነገር አይረሱትም፡፡ በእምነት ደገፉ የ5 ዓመት ህፃን ነው። ይህ ህፃን ሁለቱም ኩላሊቶቹ ደም ስለማያጣሩ ሀኪም ቤት እየተወሰደ ደሙ እየተለወጠ ነው እስካሁን በሕይወት የቆየው፡፡ ሁሉም የትንሷ ከተማ ነዋሪዎች ወደ ከሚሴ ከተማ እየሄዱ ለህፃኑ ደም ለግሰዋል፡፡ አሁን በመንደሯ ለበእምነት ደም ያልሰጠ ሰው የለም፤ ሁሉም ተዳርሷል፡፡ እባካችሁ ወደ አዲስ አበባ ስትመለሱ ልጄ ዘላቂ ህክምና አግኝቶ፣ ህይወቱ ሰንብታ አድጎና ተምሮ ለአገሩ ቁም ነገር የሚሰራ ልጅ አድርጉልኝ ሲሉ ተጓዦቹን ተማፀኑ፡፡ ተጓዦቹም በሰሙት ነገር ልባቸው ክፉኛ ተነካ፡፡ በተለያዩ ሚዲያዎች በእምነት ያለበትን ሁኔታ ለኢትዮጵያ ህዝብ ገልፀው ሁሉም የአቅሙን እንዲረዳ በማስተባበር የህፃኑን ህይወት ለመታደግ ቃል ገቡ፡፡
ህፃኑን መርዳት የምትፈልጉ በኢትዮጵያ ንግድ ባንክ የከሚሴ ቅርንጫፍ ሂሳብ ደብተር ቁጥር 10000714572347 ያስገቡለት፡፡ የእናቱ ስም አትክልት እሼቱ ይባላል፡፡

ከፍተኛ ተሰጥኦ እንዳላት የሚነገርላት የኢትዮጵያ ጃዝ አቀንቃኝ የሺ ደምመላሽ በሚያዝያ ወር አጋማሽ ላይ በኒውዮርክ የሙዚቃ ኮንሰርት እንደምታቀርብ ታዲያስ መፅሄት ዘግቧል፡፡
የጃኖ ባንድና የጂጂን ሥራዎች ያሳተመው የኒውዮርኩ ፕሮዱዩሰር ቢል ላስዌል “ፋኖ” የተሰኘ ዘፈኗን ዳግም አዋህዶ እያቀናበረላት ሲሆን የሺ አዲስ አልበም ከላስዌል ጋር የመስራት ዕቅድ እንዳላት ታውቋል፡፡
ድምፃዊቷ የኒውዮርክ ኮንሰርቷን የምታቀርበው ከ “ቅኔ” ባንድ ጋር ነው ተብሏል። በኢትዮጵያ አይዶል ዳኝነቷ የምትታወቀው የሺ፤ ከያሬድ ሙዚቃ ት/ቤት በፍሉትና በተጓዳኝ በፒያኖ አጨዋወት ተመርቃለች፡፡ አርቲስቷ “ቅኔ” የተሰኘ የመጀመርያ አልበሟን የዛሬ ሁለት ዓመት ለጆሮ ማብቃቷ ይታወሳል፡፡   

የአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ የሕግ ት/ቤት የ50ኛ ዓመት ኢዮቤልዩ በዓሉን አስመልክቶ ብሔራዊ የምስለ ችሎት ውድድር እንደሚያካሂድ ገለፀ፡፡ ከመጋቢት 16-18 የሚካሄደው ውድድር፤ በአለም አቀፍ ወንዞች አጠቃቀም ዙሪያ የተዘጋጀ ሲሆን በአገሪቱ ያሉ የሕግ ት/ቤቶች በሙሉ ይሳተፋሉ ተብሏል፡፡ የመጨረሻ የዋንጫ ውድድር መጋቢት 18 ከጠዋቱ 2፡30 ሰዓት የሚከናወን ሲሆን በጉዳዩ ላይ ከፍተኛ ምርምር ያደረጉ ምሁር በአገራችን ድንበር ተሻጋሪ ወንዞችን አስመልክቶ ስለሚነሱ የህግ ክርክሮች የማጠቃለያ ንግግር እንደሚያደርጉ የህግ ት/ቤቱ ጠቁሟል፡፡

በደሳለኝ ግርማ (ዲዶስ ሳምናስ) የተፃፉ የአጭር ልብወለድ እና የግጥም ስብስቦችን የያዘ መፅሃፍ በዛሬው ዕለት በሐረር ይመረቃል፡፡
በአንድ በኩል “አድናቂው” በሚል ርዕስ የአጭር ልብወለድ ስብስቦች ያካተተው መፅሃፉ፤ በሌላው በኩል “እግዜርና አፍሪካ” በተሰኘ ርዕስ የግጥም ስብስቦችን ይዟል፡፡ በኤች ዋይ ኢንተርናሽናል የህትመት ሥራ ድርጅት የታተመው መፅሃፉ፤ በ40 ብር ከ50 ለገበያ ቀርቧል፡፡

የፈጠራ ስራዎች ፀረ-ፊውዳል ድርሰቶች አይደሉም የሚል ምሁር ከመካከላችን ይኖራል? ታዲያ ፀረ-ፊውዳል ታጋዩና የመሬት ላራሹ መፈክር አንጋቢው ተራማጁ የተማሪዎች ማህበር ይህን ህዝባዊ ደራሲ ሳያጎላው ያለፈው ሆን ብሎ ይሆን ወይስ ረስቶት?

ይህን ጽሑፍ ያዘጋጀሁት ስለ አንጋፋው ደራሲ አቤ ጉበኛ አንዳንድ ሃሳቦችን ለመሰንዘር ነው። ጽሑፉ ከምርምርም በሉት ከጥናት ሥራ ጋር የሚመደብ አይደለም፡፡ ወፍ በረር ወይም ወፍ ዘለል ምልከታ አይባልም፡፡ በአጭሩ እኔ ስለአቤ የተሰማኝን የገለጽሁበት መላምታዊ ስሜት ነው፡፡
አቤን እኔ በሚገባ ወይም በቅርበት አላውቀውም፡፡ የአቸፈር ሰው መሆኑን፣ ዳንግላ መማሩን የተረዳሁት በቅርቡ ነው፡፡ የእኛ ዘመን ምሁራን “የየት አገር ሰው ነህ?” ተባብለው በይፋ አይጠያየቁም ነበር፡፡ በትምህርት ቤት ዘመኔ “ሰይፈ-ነበልባል” የተባለውን ድርሰቱን ያነበብሁ ይመስለኛል፡፡ በእኔ የጉርምስና ዘመን፣ በእኔ አካባቢ ስሙ እንደ ሌሎች ደራሲዎች ጎልቶ ሲነገር አልሰማሁም፡፡ ወይም የግንኙነት አድማሴ ጠባብ ነው ወይም በጆሮዬ ተኝቼበታለሁ፡፡ አሁን ይህን እያልሁ ያለሁት በዚያ በእኔ ዘመን ላይ ቆሜ መሆኑን ልብ ይሏል፡፡ አዎ! እንደ ከበደ ሚካኤል፣ እንደ መንግስቱ ለማ፣ እንደ ፀጋዬ ገ/መድህን፣ ሌላው ቢቀር እንደ መንግስቱ ገዳሙ እንኳ በስሙ አይዘመርለትም ነበር፡፡ የፈጠራ ስራው የወረደ ስለሆነ? ፈፅሞ አይመስለኝም፡፡ ሥራዎቹማ! እሳት ጫሪ፣ አነጋጋሪ፣ የአብዮት ማዕበል ጠሪ ነበሩ፡፡ ፀባዩ ከሰው ስለማይገጥም? ይህ በከፊል እውነት ሊሆን ይችላል፡፡ አቤ እከክልኝ-ልከክልህን የማያውቅ በራሱ የሚተማመን የቀለም ሰው ነበር፡፡ ይህን ሁሉ የሆነ ደራሲ ለምን ደመ መራራ ሆነ? መልሱን እኔም አልሰጣችሁም፤ እናንተም እንድትመልሱልኝ አልፈልግም፡፡
በእነዚያ ዘመናት በአቤ ስም ላይ የተጫኑትን ቋጥኞች ከሥር መሰረታቸው ፈልፍሎ ለማወቅ በእርግጥም ጥልቅ ጥናትና ምርምር ይጠይቃል፡፡ እኔ ግን መላምቴን ጎን-ለጎን ባስሔድ ጆሮውን የሚነፍገኝ እንደማይኖር ተስፋ አለኝ፡፡
1. አቤና የአጼው ዘመን
በዚያን ዘመን የነበሩ ደራሲያን፣ አብዛኛዎቹ በቀኝ እጃቸው ብዕር፣ በግራ እጃቸው ሥልጣን የጨበጡ ናቸው፡፡ በዚህም መሰረት የዘመኑ ሹም የሰራው ብቻ ሳይሆን በሩቁ በማንኪያ የነካው ወጥ ሁሉ ይጣፍጥለታል፡፡ ለምን ቢሉ? ወጡ እንዳይጎረና ዙሪያ ከበው የሚያማስሉለት ብዙ ሌቄዎች ከጎኑ ስላሉ … የዚያ ሁሉ ወጥ አማሳይ እጅ ያረፈበት ወጥ ደግሞ በየትኛውም መመዘኛ ሲታይ ላይጣፍጥ አይችልም፡፡
አቤ በዚያን ዘመን የግሽ-አባይ ጎርፍ ከገጠር አምጥቶ ከቀለጠው ከተማ የዶለው ብቸኛ ፍጡር ይመስለኛል፡፡ በቀኝ እጁም የያዘው ብዕር ብቻ ነው፡፡ ብዕሩም በቅኔ ቤት እንጂ በገነተልዑል ግቢ ውስጥ ገብቶ ያልተሟሸ ነው፡፡ ቃላቱም ቱባ-አገራዊ ሽካራ እንጅ ቤተመንግሥታዊ ለስላሳ አይደለም፤ አስተሳሰቡም ደረቅ-ገጠራዊ እንጅ ከተማዊ-ጮሌ አይመስለኝም፡፡ ገፀ-ባህርያቱም አብዛኛዎቹ ከውጭ አገር የኮረጃቸው ሳይሆን ከአካባቢው በተጨባጭ የፈጠራቸው ናቸው። በፖለቲከኞች ቋንቋ ለመናገር፣ አቤ ለዘመኑ ቢሮክራሲ አጎብዳጅ አልነበረም። (አስር ጊዜ አይመስለኝም… ይመስለኛል… የምለው ያለምክንያት አይደለም፡፡ አንድም ከላይ እንደገለጽሁት ጽሑፉ ጥናታዊ አለመሆኑን ለማረጋገጥ ነው፡፡ ሁለትም ለዚህ መረጃ የሚሆን ማጣቀሻ የፈረንጅ ስም ለመጥራት ስላልፈለግሁ ነው፡፡ ሶስትም አገራዊ ሊቃውንትን በመረጃነት እንዳላቀርብ የቀሰምሁት ዘመናዊ የፈረንጅ ትምህርት የሚስበኝ ወደ ነጭ ምሁራን እንጂ ወደ እራሴ ሊቃውንት አለመሆኑን ለማስገንዘብ ጭምር ነው፡፡)
ወደ ተነሳሁበት ነጥብ ልመለስ፡፡ እና! የአቤ ስም በዘመነ አፄ ለምን ገንኖ አልወጣም? ልብ በሉ፤ አቤ በዚያን ዘመን ግራ እጁ ባዶ ቢሆንም ቀኝ እጁ የሚንቦገቦግ የብዕር ሰይፍ ጨብጧል፡፡ ይህ ሰይፈ-ነበልባል የዘውዱን ህዝባዊ የብዕር ሰው ስም በስርአቱ እንዲታፈን መደረጉ ተገቢም ባይሆን የሚጠበቅ ነው፡፡ ያኔ ሥዩመ እግዚአብሔርን መዳፈር ራሱን ፈጣሪን መድፈር ሆኖ ይቆጠራል፡፡ ይህንን የስዩማንን ድፍረት ቅኔ የቆረጠባት ቤተክርስቲያንም ብትሆን በደግ የምትቀበለው አይመስለኝም፡፡ ቀብታ ያነገሰችውን ንጉሥ ከጉያዋ የወጣ ደብተራ፣ በግራ እጁ ስልጣን ያልጨበጠ ብዕረኛ፣ የቁም-ስቅሉን ሲያበላው ቁጭ ብላ አትመለከተውም፡፡ ያኔ! አቤን አውግዢው፤ ወይም የይቅርታ ደብዳቤ አስጽፊው ብትባል አቤን እንዲጽፍ ሳታስገድደው የምትቀር አይመስለኝም፡፡
ንጉሡና በእሳቸው አካባቢ ያሉት መኳንንትና መሳፍንት አቤን የሚመለከቱት እንደ ኮሚኒዝም በጎሪጥ ነው፡፡ በዘመነ አብዮት ቆምጬ፤ “ኢምፔሪያሊዝምን በጎሪጥ ሶሻሊዝምን እንደ በላይ ዘለቀ አያቸዋለሁ” ብሏል አሉ፡፡ ይህ በዘመኑ ቢሮክራሲ የጎሪጥ የሚታይ ሰው፣ ግራ እጁ ባዶ የሆነ፣ ብዕሩ አርፎ የማይተኛ ተንኳሽ፣ በዐይነ-ቁራኛ የሚታይ ሞገደኛ ብዕረኛ፣ እንኳንስ ስም አሞጋሽ፣ አፍ-አካፋች ጓደኛም አይኖረውም፡፡ እንኳንስ በቀኛቸው ብዕር፣ በግራቸው ሥልጣን የጨበጡት ደራሲያን፣ የእነሱ ቅርበት ያላቸውም ንዑስ ደራሲያንም ቢሆኑ አቤን የሚቀርቡ አይመስለኝም፡፡ ከእሱ ጋር መታየት ከእሱ ጋር መፈረጅ ነው፡፡ ከእሱ ጋር መፈረጅ ደግሞ ከእሱ ጋር ግዞት መውረድ ያስከትላል፡፡ በመሆኑም በዘመኑ አቤን የከበቡት ስም አጥፊዎቹ እንጅ ስም አልሚዎቹ አይደሉም ባይ ነኝ፡፡ በቀረው ተመራማሪው ይሙላበት፡፡  
2. አቤና የተማሪው እንቅስቃሴ
እንደሚታወቀው የኢትዮጵያ ተማሪዎች እንቅስቃሴ በአገራችን ብቻ ሳይሆን በመላው ተራማጅ ዓለም ህዝቦች ዘንድ አንቱ የተባለ ማህበር ነበር፡፡ ማህበሩ ጥልቅ ተራማጅ ብቻ ሳይሆን የሶሻሊስት ርዕዮት አለም ተከታይ ጭምር ነበር፡፡ እንቅስቃሴውም በአገር ውስጥ የነበረው ተሰሚነት ቀላል አልነበረም፡፡ የዘውዱን ስርዓት ቦርቡሮ የጣለው ይህ እንቅስቃሴ እንደሆነ ይታመናል፡፡ ምንም እንኳ ዋርዳ ወይም ማማት ወፎች ፈልገው ያገኙትን የሾላ ፍሬ (አብዮት መሆኑ ነው) አንድ ጉራሽ ሳይቀምሱት ዛፉ ላይ ወጥተው ሲንጫጩ፣ የቤተ መንግሥት ጫካ ተንተርሶ፣ እረኛ መስሎ የበግ ለምድ ለብሶ፣ ያደፈጠ ዝንጀሮ የሾላውን ፍሬ ቢቀማቸውም፣ የተማሪው እንቅስቃሴ ለዚያን ጊዜው ለውጥ ያበረከተው አስተዋጽኦ እጅግ ከፍተኛ ነበር፡፡
ይህ እንቅስቃሴ በላይን ንጉሡ አንቀው ከቀበሩት ጉድጓድ አውጥቶ የታጋይ ካባ ያለበሰ ማህበር ነው። ደጃዝማች ታከለን ፈርጣጭ ንጉሥ አጋች ብሎ ያሟካሸ ነው፡፡ ከዘመኑም ደራሲያን መካከል መርጦ የተቡ ብዕርተኞች ብሎ የካበና የሾመ ነው፡፡ ለ“አልወለድም” ደራሲ፣ በግራ እጁ ባዶ ሆኖ ሥርዓቱን ቀድሞ ለተፋለመ ህዝባዊ የብዕር ሰው፣ ማህበሩ ለምን ያኔ! የጎላ ዕውቅና አልሰጠውም? በግሌ ይህ ተራማጁ የተማሪዎች እንቅስቃሴ በመጽሔቶቹ ላይ ስለ አቤ የፃፈውን ነገር አላነበብሁም፡፡
አቤ በሩሲያ ሥነ-ጽሑፍ ውስጥ ሥራው በተራማጅነት ተፈርጆ ሰፊ መድረክ ሲሰጠው፣ ተራማጁ የተማሪው ማህበር ለምን ስለአቤ ምንም ሳይል አለፈ? አቤ የተማሪው ማህበር የቆመለተን ዓለማ ሙሉ-በሙሉ ያሟላ ብዕረኛ ነው፡፡ የዘውድን ሥርዓት በብዕሩ በጽናት ተፋልሟል፡፡ ለዚህም ድፍረቱ ተግዞ ታስሯል፡፡ ከዘመኑ ብዕረኞች መካከል እንደ አቤ የዘውድ ስርዓትን በብዕሩ በግልጽ የሞገተ ደራሲ እንኳን ያኔ፣ አሁንም ያለ አይመስለኝም፡፡ ታዲያ፣ ጉዳዩ ይህ ሆኖ ሳለ፣ በዓላማ የተሳሰረውን ህዝባዊ ደራሲ፣ ተራማጁ የተማሪዎች ማህበር ለምን ስሙን ሊያገነው አልቻለም? እውን “አልወለድም”ን ባያነብ ነው? ሠይፈ ነበልባልን አንብቦ ባይገባው ነው? ቢያንስ “አንድ ለእናቱ” ብቻውን የአቤን ስም ማግነን ይሳነዋል? የዳኛቸው ወርቁን ብቸኛ ልብወለድ “አደፍርስ”ን በየጥናት ክበባት ያስነበበን የተማሪ ማህበር፣ ለምን ከአቤ ስራዎች አንዱን እንድንወያይበት አላደረገም? የአቤስ የፈጠራ ስራዎች ፀረ-ፊውዳል ድርሰቶች አይደሉም የሚል ምሁር ከመካከላችን ይኖራል? ታዲያ ፀረ-ፊውዳል ታጋዩና የመሬት ላራሹ መፈክር አንጋቢው ተራማጁ የተማሪዎች ማህበር ይህን ህዝባዊ ደራሲ ሳያጎላው ያለፈው ሆን ብሎ ይሆን ወይስ ረስቶት? መልሱን ባውቀውም አልነግራችሁም፡፡ እናንተም እንድትነግሩኝ አልፈልግም፡፡ ለምን ብትሉ መላምት እንጅ ጥናትና ምርምር አይደለምና፡፡
3. አቤና ደርግ
“ሶሽያሊስት ነኝ” ያለው የደርግ መንግሥት ሶሽያሊስት አመለካከት ላላቸው የጥበብ ሰዎች ወዳጅ አልነበረም፡፡ ማርክስ ለማለት ማርቆስ የሚሉትን የደርግ አባላት ያስተካከሏቸው ደብተራቸውን ወርውረው፣ ትምህርታቸውን ጥለው ለዘመናት የታገሉለት አብዮት በእርግጥ የፈነዳ መስሏቸው አገር ቤት የገቡት፣ የተማሪውን ማህበር ሲያንቀሳቅሱ የኖሩት እውነተኛ ተራማጆ ናቸው፡፡ እነዚህም ወጣት ተራማጆች በወጉ ሳይደራጁ አገር ቤት ገብተው ደርግ እርስ-በእርስ ያጨፋጨፋቸውና የተረፉትን እራሱ አርዶ አስፋልት ላይ ያሰጣቸው ናቸው፡፡ በአጭሩ ኮትኩተው-አሰልጥነው፣ መግበው ያሳደጉት ውሻ የበላቸው የዋህ ታጋዮች ናቸው፡፡
ወደ አቤ ስመጣ፣ ደርግ በአብዮት ስም የተረከባት አገር እነአቤ ቀደም ብለው በህዝባዊ ብዕራቸው ያደነቋት፣ የዘመሩላት፣ የተጋዙላት ኢትዮጵያ ናት፡፡ እጅግ በርካታ ህዝቦች አንድ-አንድ ጡብ እየጨመሩ በገነቡት ቤት ላይ ደርግ የመጨረሻዋን ጡብ እንኳ ሳያሰቀምጥ የቤቱ ባለቤት እኔ ነኝ አለ፡፡ በእርግጥም ደርግ ምንም አይነት ጡብ በዚህ የቤት ሥራ ላይ አላኖረም፡፡ በአንፃሩ ግን ደርግ በዘውድ ሥርዐት ታማኝነቱ፣ በአጣና ደብዳቢነቱ፣ በግድያ ፈፃሚነቱ፣ ሕንፃ ገንቢ የሆኑ ተማሪዎችን፣ ምሁራንን በአጠቃላይ ምስኪን ገበሬዎችን አሳዶ ይገድል፣ ህዝባዊ የፈጠራ ሰዎችን ያስር፣ ከግዞት እንዳይወጡ በር ዘግቶ ይጠብቅ የነበረ ዋርድያ ነው፡፡ ይህ ዋርድያ የአገሪቱን ስልጣን ከተረከበበት ቀን ጀምሮ በአፉ ሶሻሊዝም እየሰበከ፣ በተግባር ሶሽያሊስት አመለካከት የነበራቸውን የጥበብ ሰዎች ከኢምፔሪያሊዝም ጋር ደምሮ የጎሪጥ ያያቸው ጀመር፡፡ እንደ አቤ ባይበረታባቸውም መንግስቱ ለማና ሌሎችም የደርግ ጥላቻ ዒላማ ነበሩ፡፡
የአቤ ድርሰቶች ለደርግ የተዋጡለት አይመስልም። ለስልጣን ወይም ለገንዘብ የማይንበረከከው አቤ፤ ከጊዜ በኋላ ብዕሩን ወደ ደርግ እንደሚያዞርበት ገብቶታል፡፡ ደርግ የጀመረውን ትውልድ የማጥፋት ዘመቻውን አቤ ዐይቶ እንዳላየ፣ ሰምቶ እንዳልሰማ ሆኖ በፀጋ የሚቀበለው አይሆንም። በዚህም መሰረት አቤን ከአካባቢው አርቆታል፡፡ የ“አልዋለድም” ደራሲ ጭራሮ-እንጨት ሆኖ ያቀጣጠለውን የአብዮት እሳት ቀርቦ እንዳይሞቅ አግዶታል፡፡ ምንም ዐይነት አስተዋጽኦ እንዳላደረገ ሆን ብሎ ወደ ጎን ገፍቶታል። ዛሬም እንደ ትላንቱ አቤ ከሁሉም የተገለለ ብቸኛ ደራሲ ሆኗል፡፡ ዛሬም እንደ ትላንቱ በጃንዳርም ሰላዮች የሚጠበቅ የብዕር ሰው ተብሏል፡፡ ከአቤ ጋር ቆሞ መታየት ሳይቀር ቀይ ሽብርን የሚጋብዝ አስፈሪ ጉዳይ ሆኗል፡፡ የእሱን ብዕር ምርኳዝ አድርገው ሥልጣን ላይ የወጡ ደርጎች ለምን የአቤ ስም እንዲቀበር ፈለጉ? በእርግጥም አቤ በወቅቱ የደርግ ስጋት ነበረ? አዎ! ነበረ፡፡ ምንአልባት በወቅቱ የፈለቁት ሕቡዕ ድርጅቶች መልምለውት ይሆን? ጨርሶ አልተጠጉትም፡፡ አቤ ከእነሱ ሁሉ ባላይ አርቆ የሚያስብ ታጋይ ብዕረኛ ነበር፡፡ አሁን አጠገቤ ቢሆን ኖሮ “ማንም ተልካሻ በተጠራበት ስም ታጋይ፣ ተራማጅ፣ አትበለኝ” ብሎ ይገስፀኝ ነበር፡፡ አቤ ያኔ! ወደ አንዱ ጎራ ጠባ ቢልማ ኑሮውና ቀብሩም የውሻ ባልሆነ ነበር፡፡
የተፋለመለትን ህዝብ አምኖ ለህዝብ መብትና ፍትህ እየጮኸ፣ የተጋዘለት ህዝብ ግን ሳይደርስለት ደሙ-ደመ ከልብ ሆኖ ቀረ፡፡
እና! በፈጣሪ ተሰይሞም ሆነ ጠበንጃ አንግቦ ሥልጣን ላይ የወጣ ሹም ሁሉ ለምን አቤን ጠላው? ለምን አሳደደው? ለምን ሊቀበር የማይችለውን ስሙን ለመቅበር ሞከረ? መልሱን እኔም አልነግራችሁም … እናንተም እንድትመልሱልኝ አልፈልግም፡፡ ጥያቄ?

Saturday, 08 March 2014 13:00

የቀልድ - ጥግ

ትርጓሜ
ጉባዔ፡- ጉባዔ ማለት ታዋቂ ሰዎች ለየብቻቸው ሊሠሩት የማይችሉትን ነገር አንድ ላይ ሆነው በቃ ምንም ሊሠራ አይቻልም ብለው ተስማምተው የሚወስኑበት ስብሰባ ነው፡፡
*   *   *
አንድ ታላቅ ባለሥልጣን ጉባዔን ሲገልፁት፤ “ጉባዔ ማለት የአንድ ሰው መደናበር በተሰብሳቢው ቁጥር ሲባዛ የሚገኝ የስብስብ ብዛት ነው!”
*   *   *
የ25ኛ ዓመት የጋብቻ ቀኑን የሚያከብር አንድ ባል በጣም ተደብሮ ያየው ጓደኛው ሊያፅናናው እየሞከረ ሲያባብለው፤ ባልዬው ብስጭቱን ሲገልፅ እንዲህ አለ፡-
“በ5ኛው የጋብቻ በዓላችን ጊዜ ሚስቴን ልገድላት አስቤ ጠበቃዬን ባማክረው “20 ዓመት ያስፈድርብሃል ተው” ብሎኝ ተውኩ፡፡ እስቲ አስበው ወዳጄ! ይሄኔኮ ከእሥር ቤት ወጥቼ ነበር!”
*    *   *
ዳኛ (ለተከሳሹ)፡- “በአራት አመት ጥብቅ እሥራትና ከአገር እንድትባረር ተፈርዶብሃል፡፡ የምትለው ነገር አለህ?”
ተከሳሹ፡- “ጌታዬ ሁለተኛው ውሳኔ መጀመሪያ ይሁንልኝ!”
*   *   *
ዳኛ፡- “ፍርድ ቤቱ ውሳኔ ከማስተላለፉ በፊት የምታቀርበው ነገር አለ?”
እሥረኛ፡- “ኧረ ምንም የለኝ ጌታዬ! 50 ብር ነበረኝ ጠበቃዬ ወሰደው”
*   *   *
ሴትዮዋ አዋቂ ዘንድ ሄዳ ዕጣ-ፈንታዬን ንገረኝ ትለዋለች፡፡
አዋቂ፡- (መዳፏን እያየላት) አንድ ረዥም ጥቁር ሰውዬ መጥቶ ሲያሳልፍሽ ይታየኛል፡፡”
ሴትዬዋ፡- “ምን ምን ያደርግልኛል ጌታዬ?”
አዋቂ፡- “ስጦታ በስጦታ ያደርግሻል፡፡ ናይት ክለብ ወስዶ አለምሽን ያሳይሻል፡፡ ፍቅር ለዘለዓለም ይኑር! ብለሽ ዋንጫሽን ታነሺለታለሽ”
ሴትዬዋ፡- “ጥቁሩ ሰውዬ ብዙ ገንዘብ አለው ጌታዬ?” አለች ሴትዮዋ ፍንክንክ እያለች፡፡”  
አዋቂ፡- “ምን ነካሽ? ሰውዬውኮ የአንድ ትልቅ ኩባንያ ፕሬዚዳንት ነው፡፡ ከእናት አባቱ 900,000 ብር የሚከራይ አፓርትማ ወርሷል”
ሴትዮዋ፡- “ታድዬ! እንዴት ያለ ፀጋ ፈሰሰልኝ ጌታዬ! አንድ ነገር ብቻ እንድጠይቅዎ ይፍቀዱልኝ ጌታዬ?”
አዋቂ፡- “ጠይቂኝ!”
ሴትዮዋ፡- “ባሌንና ሶስቱን ልጆቼን የት አረጋቸዋለሁ? ምን ይውጣቸዋል?”

ስለማኅበራት የሰጡትን አስተያየት መልሰው እንዲያጤኑት ተጠየቀ
‹‹ማኅበራት በትኩረት ሊመሩና ጉዟቸውም እየተፈተሸ ሊስተካከል ይገባል›› - መንግሥት


የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ፓትርያርክ ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ‹‹ከዩኒቨርስቲ ተመርቀው ቤተ ክርስቲያንን እንምራ እያሉ ነው፤ ቤተ ክርስቲያኒቱ ትውፊትና ሥርዓት አላት፤እንዲህ ማለት አይችሉም›› በማለት የሰጡትን አስተያየት መልሰው እንዲያጤኑት በንግግራቸው ቅር የተሰኙ የመንፈሳውያን ማኅበራት አገልጋዮች ጠየቁ፡፡
አገልጋዮቹ ለአዲስ አድማስ እንደተናገሩት፣ አቡነ ማትያስ ይሄን አስተያየት የሰነዘሩት በመንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ቤተ ክህነት ጽ/ቤት የስብከተ ወንጌልና ሐዋርያዊ ተልእኮ መምሪያ ከኢትዮጵያ መጽሐፍ ቅዱስ ማኅበር ጋር በመተባበር የካቲት 21 እና 22 ያዘጋጁት ሀገር አቀፍ የስብከተ ወንጌል የምክክር ጉባኤ በተካሔደበት ወቅት ነው፡፡
በምክክር ጉባኤው መዝጊያ ላይ ባደረጉት ንግግር ‹‹በባዮሎጂና ኬምስትሪ እንቀድስ እያሉ ነው፤›› ያሉት አቡነ ማትያስ፤ ‹‹ምን እያልኹ እንደኾን ይገባችኋል›› በማለት ማንን እንደሆነ የማሳየት ያህል የጠቆሙበት አስተያየት ያልተለመደና ጥቂት የማይባሉ የጉባኤውን ተሳታፊዎች ያሳዘነ እንደነበር የጉባኤው  ምንጮች አመልክተዋል፡፡
በምክክር ጉባኤው ላይ ለውይይት በቀረቡ ጽሑፎች፣ እስከ ሰማንያ ሺሕ የሚገመቱ መንፈሳውያን ማኅበራት በቤተ ክርስቲያኒቱ ስም በአዲስ አበባ እንደሚንቀሳቀሱ የተጠቀሰ ሲሆን  ቤተ ክርስቲያኒቱ ማህበራቱ በሕግና በሥርዐት የሚመሩበት ደንብ አውጥታ እስካልተቆጣጠረቻቸው ድረስ እየተከሠቱና ሊከሠቱ የሚችሉ ችግሮች በቀላሉ እንደማይታዩ ተመልክቷል፡፡
ቅሬታ አቅራቢዎቹ በበኩላቸው፤በማኅበር ሽፋን ለግል ጥቅማቸውና ፍላጎታቸው የሚሯሯጡ፣ የሃይማኖትና የሥነ ምግባር ሕጸጽ የሚታይባቸው ማኅበራት የመኖራቸውን ያህል ጥሩ ሥነ ምግባር ያላቸው፣ ምእመናንን በማትጋት ለበለጠ ሀብተ ጸጋ የሚያበቁ ጠንካራ ማኅበራትም እንዳሉ ገልጸዋል፡፡  ከቅርብ ጊዜ ወዲህ በምክክር መድረክና በቤተ ክህነቱ ጉባኤያት እየታየ ያለው “ማኅበራት አላሰራ አሉን” በሚል በጅምላ የመፈረጅና የመኰነን ዝንባሌ፣ አብዛኞቹ ማኅበራት ለሀገርና ለቤተ ክርስቲያን እያበረከቱ ያለውንና  በቤተ ክህነቱ ቀጥተኛ አቅም ሊሸፈን የማይችለውን ዘርፈ-ብዙ አገልግሎት ያላመዛዘነ ነው ብለዋል -የማህበራት አገልጋዮች፡፡
“በአሁኑ ጊዜ ማኅበራት የአባሎቻቸውንና የበጎ አድራጊ ምእመናንን የገንዘብ፣ የዕውቀትና ሞያዊ አቅም በማስተባበር የገጠር አብያተ ክርስቲያናት፣ ገዳማት፣ አድባራትና የአብነት ት/ቤቶች በተቀናጀ መንገድ እንዲረዱ ያደርጋሉ፤ ለቤተ ክርስቲያንና ለሀገር ዕድገት የሚጠቅሙ ልዩ ልዩ ጥናቶችን ያካሒዳሉ፤ በጠረፍ የሀገሪቱ ክፍል በሚያከናውኑት የስብከተ ወንጌል እንቅስቃሴ ምእመኑ በቋንቋው የሚገለገልበትን ኹኔታ ያመቻቻሉ፤ የቅዱሳት መካናት ተሳላሚዎችን ጉዞ በማስተባበር ሕዝቡ ቅርሱንና ባህሉን አውቆ እንዲጠብቀውና እንዲከባከበው ከማስቻላቸው ባሻገር ለሀገር ውስጥ ቱሪዝም መስፋፋትና መጠናከርም ያላቸው አስተዋፅኦ በቀላሉ የሚታይ አይደለም፡፡” ሲሉ የማህበራትን ጥቅም አብራርተዋል፡፡
ማኅበራቱ አብዛኞቹን ተግባራት የሚያከናውኑት በየደረጃው ከሚገኙ የቤተ ክርስቲያኒቱ ሓላፊዎች ፈቃድ እያገኙና መመሪያ እየተቀበሉ መኾኑን የሚገልጹት አገልጋዮቹ፣ በግንቦት 2004 ዓ.ም. የማኅበራትን ቁጥር ስለመቆጣጠር ለቅዱስ ሲኖዶስ ቀርቦ በነበረው ጥናት መነሻነት ምልዓተ ጉባኤው ራሱን የቻለና ማኅበራቱን የሚያሠራ ሕግ እንዲዘጋጅ ሊቃነ ጳጳሳት፣ ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያንና የሕግ ባለሞያዎች ያሉበት ደንብ አዘጋጅ ኮሚቴ ሠይሞ እንደነበር ያስታውሳሉ፡፡ የማኅበራት አደረጃጀትና የፋይናንስ ቁጥጥር መርሕን ጠብቆ እንደሚወጣ ሲጠበቅ የቆየው ደንብ ከሚገባው በላይ መዘግየቱ ችግሩ ከቤተ ክህነቱ እንጂ ከማኅበራቱ አገልግሎትና ብዛት አለመኾኑን እንደሚያመለክት ይከራከራሉ፡፡
ፓትርያርኩ አድልዎ በሌለው መልኩ ቤተ ክርስቲያኒቱን ለማስተዳደር በዕለተ ሢመታቸው ቃለ መሐላ መፈጸማቸውን የሚናገሩት ቅሬታ አቅራቢዎቹ፣ በምክክር ጉባኤው ላይ በተጠቀሰው አኳኋን የመናገራቸው ግፊት የተለያየ መነሻ ሊኖረው እንደሚችል አስተያየታቸውን ሰንዝረዋል፡፡
የመጀመሪያው መንሥኤ፣ የሙስናንና ብልሹ አሠራርን ችግር ለመቅረፍና ለማድረቅ በቅ/ሲኖዶስ ምልዓተ ጉባኤ ውሳኔ መሠረት ለአዲስ አበባ ሀ/ስብከት የተሠራው የመዋቅር፣የአደረጃጀትና የአሠራር ጥናት ተቃዋሚዎች የጥናቱ ባለቤት ነው በማለት በሚከሡት ማኅበረ ቅዱሳን ላይ በቤተ ክርስቲያኒቱ ከፍተኛ አመራር አማካይነት እንዲፈጠር የሚሹት ጫና ነው፡፡ ኹለተኛው ደግሞ በመንግሥት በኩል፣ ‹‹በኦርቶዶክስ ሃይማኖት ውስጥ አክራሪነትና ጽንፈኝነት የሚታየው ህልውናቸውና ዓላማቸው ሃይማኖታዊና በሃይማኖቱ የበላይ ጠባቂዎች ይኹንታ በተቋቋሙ የወጣት ማኅበራት አደረጃጀቶች ውስጥ በመሸጉ አካላት ነው፤ ስለዚህም ማኅበራት በትኩረት ሊመሩና ጉዟቸውም እየተፈተሸ ሊስተካከሉ  ይገባል፤›› የሚለው ክሥ በመሪዎቹ ላይ ያሳደረው ማኅበራቱን የመቆጣጠር ጫና ነው፡፡
የአክራሪነትንና ጽንፈኝነትን ምንነትና መፍትሔዎችን በሚተነትኑት የመንግሥት ሰነዶች፣ የሃይማኖት ተቋማትን ለአክራሪነትና ጽንፈኝነት ተጋላጭ ያደርጋቸዋል ከሚባሉት ኹኔታዎች ውስጥ÷ የሃይማኖት ተቋማቱ የሰው ኃይል አስተዳደርና የፋይናንስ ሥርዐት ለተከታዩ ሕዝብ ግልጽነትና ተጠያቂነት የሌላቸው መኾናቸው፣ በሙስናና በአስተዳደር በደል ሳቢያ የሚፈጠር ግጭት፣ የሰው ኃይል አስተዳደር በዘመድ አዝማድና በጉቦ እየኾነ የሥራ ብቃት በሌላቸው ሰዎች የሚሠራበት፣ የኦዲት ሪፖርት ቀርቦ የሚተችበትና አስተያየት የሚሰጥበት ሥርዐት አለመዳበሩ፣ ተከታዮችን አክራሪነትን የሚቋቋም በሃይማኖት ዕውቀት የማስታጠቅ ክፍተት ይገኙበታል፡፡
በመንግሥት ትንታኔ መሠረት፣አክራሪነትን የመዋጊያው ቁልፍ መሣሪያ ልማትንና ዕድገትን በማፋጠን የመልካም አስተዳደር ችግርን መቅረፍ፣ሕዝቡን በሃይማኖታዊ ዕውቀት ማስታጠቅ ነው፡፡ የሃይማኖት ተቋማትን ለአክራሪነትና ጽንፈኝነት ተጋላጭ ያደርጓቸዋል የተባሉት የመልካም አስተዳደርና የብልሹ አሠራር ችግሮች÷ ማኅበረ ቅዱሳን በተቃዋሚዎች አላግባብ በሚከሠሥበት የመዋቅር፣ የአደረጃጀትና የአሠራር ለውጥ ጥናት ትግበራ በማፋጠን እንዲኹም ማኅበረ ቅዱሳንን ጨምሮ በርካታ ማኅበራት በመቶ ሺሕ የሚቆጠሩ የገዳማትና የአብነት ት/ቤት ማኅበረሰብን በልማትና ተራድኦ ከመደገፍ ጀምሮ በሚያከናውኑት ሐዋርያዊ ተልእኮ ንቃት ሊወገድ እንደሚችል ቅሬታ አቅራቢዎቹ ያምናሉ፡፡ ከዚኽም አንጻር ፓትርያርኩ ንግግራቸውን መልሰው በማጤን ማኅበራት አገልግሎታቸውን አጠናክረው ለመቀጠል የሚያስችላቸው ኹኔታ እንዲያመቻቹ ጠይቀዋል፡፡

ሬት በትለር (ነገም ሌላ ቀን ነው)

አንድ የፖለቲካ ምርጫ ተሳታፊ፤ ሁሌ የቆሸሸና አልባሌ ልብስ ይለብሱ ነበረ ይባላል፡፡ አደባባይ ከሚገኝ አልባሌ መሸታ ቤት እየገቡ ነበር የሚዝናኑት፡፡ ይሰክራሉ፤ የፖለቲካ ክርክር ያበዛሉ፡፡ ይሟዘዛሉ፡፡ በዚህ ምክንያት ጨዋና ደግ ነው የሚባለው መራጭ ህብረተሰብ በተመራጩ ቅሬታ ይሰማዋል፡፡ ደጋፊዎቹም በጣም ይቀየሙዋቸዋል፡፡ የህዝቡን ብሶት የሰማ፤ የተመራጩን ተራ መሆን ና ወረዳ መሆን አስመልክቶ ሊያጋልጣቸው የፈለገ አንድ የተቃዋሚ ጋዜጣ አዘጋጅ ሪፖርተሩን ይጠራና፤
“ስማ እኒህን ተመራጭ በተቻለ መጠን ተከታትለህ፤ እንዴት እንደሚደነፉ፣ የሚያገኟቸውን ሰዎች እንዴት እንደሚከራከሩ፣ የሚሳደቧቸውን ስድቦች፣ ከሚያሽኮረምሟቸው ሴቶች ጋር ምን እንደሚባባሉ፤ በደምብ አዳምጠህ ስታበቃ በመጨረሻ ቃለ-መጠይቅ ታደርግላቸዋለህ፡፡ በጥንቃቄ እንድትዘግብ” ይለዋል፡፡
ጋዜጠኛው ተመራጩ ወደሚዝናኑበት መሸታ ቤት ይሄድና እንደተባለው  አግኝቶ ሲከታተላቸው ይቆያል፡፡ በመጨረሻም፤
“ጌታዬ ኢንተርቪው ላደርግዎ ነበር?” ሲል በትህትና ይጠይቃል፡፡
“ስለ ምንድነው … ቃለ …መጠይቅ … እንድሰጥህ የፈለከው?” አሉ ተመራጩ፡፡ ድምፃቸው ክፉኛ ይንተባተባል፡፡
“በአጠቃላይ ስለ ምርጫው”
“መ..ል..ካም” አሉ በተንጀባረረ ቃና፡፡
ጋዜጠኛው ቴፑን ደግኖ ቃለ-መጠይቁን አደረገና አበቃ፡፡ የቀደመውን መልሶ አዳመጠው፡፡ ወደ ፅሁፍ ለወጠው፡፡ በጣም ደነገጠ፡፡ መንተባተብ በመንተባተብ ሆኗል፡፡ ንግግሩ ቁርጥርጥ ያለና ጭራና ቀንዱ የማይያዝ ነው፡፡ በዚያ ላይ የመጨረሻው አረፍተ ነገር አስደንጋጭ ነው፡፡
“ያልመረጥሺኝ ወዮልሽ! ዋጋሽን ታገኛለሽ!” ነበር ያሉትሰ፡፡ ጋዜጠኛው ኢንተርቪውን አርትዖት እንዲያደርግለት ለአለቃው አሳየው፡፡ አለቃውም እንደዚያው ደነገጠና፤
“በል ጠዋት ወደ ቢሮዋቸው ሄደህ የሚያስተካክሉት ነገር ካለ ይዩት በላቸው” አለው፡፡
እንደታዘዘው ጋዜጠኛው ወደተመራጩ ቢሮ ሄዶ “ጌታዬ የሚያስተካክሉት ነገር ካለ አንዴ ያንብቡት?” አላቸው፡፡ ተመራጩ በዞረ-ድምር እየተጨናበሱ፤ አነበቡት፡፡ ውልግድግዱ የወጣ ፅሁፍ ሆኖ አገኙት፡፡  ለጋዜጠኛው መልሰው ወረቀቱን ሲሰጡትሱ፤ “ስማ አንተ ጋዜጠኛ! አንድ ምክር ልስጥህ! ወደፊት በምንም ዓይነት፤ ሰክረህ ቃለ-መጠይቅ አትሥራ! ካሁን በኋላ እንዲህ እያወለጋገድህ ትፅፍና ከጐንህ ታገኛታለህ!! እኛንኮ ነው የምታሳጣን!!”
*   *   *
የዛሬውን የሀገራችንን ሁኔታ ስናየው ልማት እየተካሄደ ያለበት፤ አያሌ ሹም ሽሮች፣ የተካሄዱበት… እንደ ቴሌ፣ መብራት ኃይልና ውሃ ልማት ያሉ ድርጅቶች ተዳክመውና ድክመታቸውን ለማረም ሁነኛ እንቅስቃሴ ሲያሳዩ የማይታዩበት፣ የህዝባችን የዕለት ተዕለት ኢኮኖሚ እየደቀቀ የመጣበት … ህይወት በየአቅጣጫው ዛሬም አሳሳቢ የሆነበት፤ ባለሥልጣን ትላንት ያለውን ዛሬ የሚክድበት፣ አሊያም ትላንት የካደውን ዛሬ የሚያምንበት፤… ወደድንም ጠላንም ግን ዛሬም ኤጭ አይባል የአገር ጉዳይ የምንልበት ነው! ሁላችንንም ያገባናል! ሚዲያዎች ይህንን ሁኔታ በደከመም ሆነ በከረረ መልኩ ሁሌም ሲያሳውቁ ቆይተዋል፡፡ መረጃ ያላገኘ-ህዝብ (uninformed public) በደመ-ነብስ የሚኖር ህዝብ ይሆናልና፡፡ ሀቅን መቀበል የዲሞክራሲ የበኩር ልጅ ነው፡፡
የሀገራችንን ድክመትና ጥንካሬ የሚመለከታቸው አካላት ሊያሳውቁን ይገባል፡፡ ግልፅነት አንዱ መርሀችን ነው ብለናልና የፓርቲና የፓርቲ ግጭት፣ የፓርቲና የመንግሥት አካላት አለመጣጣም፤ የበላይ መኰንንና የበላይ መኰንን አለመግባባት፤ የአለቃና የምንዝር ፍጥጫ፤ የበዝባዥና የተበዝባዥ ህዝብ መካረር፣ የኮንትራባንዲስቶች ሻጥር፣ አሻጥርና የተከላካይ አካላት ግፍጫ፣ ሹም ሽርና የመተካካት ለውጥ፤ የአይነኬ ባለሥልጣናትና የአውቆ ዝሞች ማቀርቀር፤  … ወዘተ ሳይገለፁና ሳይታሰብባቸው ውጥረትን የሚፈጥሩ፣ ችግርን የሚያባብሱ፣ ምሬትና ብሶትን የሚያቁሩ፤ ፍሬ-ጉዳዮች ናቸው፡፡ በጥንቃቄ ሊታሰብባቸው የሚገቡ ናቸው! የእኔን ከተወጣሁ ሌላው እንደ ፍጥርጥሩ ማለት፤ አገርን ከዝብርቅርቅ ቀለምና ከተበጫጨቀ ጨርቅ ተገጣጥማ የተሰፋች ያስመስላታል፡፡
የሀገራችን ሌላው አሳሳቢ ችግር የሥራ-መቀዛቀዝ መንፈስ ነው፡፡ ዛሬም ለምን መባል አለበት፡፡ ጥቅሙ ለማን እንደሆነ የማይታወቅ ሥራ-ቀልባሽ ሂደት ነው፡፡ ያም ሆኖ የብዙ ውስጥ-ውስጡን የበሰሉና ያረሩ ምሬቶች ጥርቅም ይመስላል፡፡ የሰው-ጤፉነትና የበላይነት ስሜት (Superiority complex)ም ሆነ፣ የበታችነትና ራስን ዝቅ-አድርጐ የመመልከት አስተሳሰብ (Infiriority complex) ስሜት፤ የዴሞክራሲያዊ አመለካከት አካላት አይደሉም፡፡ የትምክህተኝነትም (Chauvenism) ሆነ፣ የጠባብ አመለካከት (Narrow Nationalist) ፈርጆች፤ የዲሞክራሲያዊ አመለካከት አካላት አይደሉም፡፡ ያለመቻቻል (Tolerance)፣ ወገንተኛነትና ተዓብዮ የዲሞክራሲያዊ አመለካከት አካላት አይደሉም፡፡ እነዚህን ሁሉ መርምሮ “ዴሞክራሲያዊ ነኝ ወይ?” ብሎ ሁሉም ራሱን በጊዜ መፈተሹ የቀኑ ጥያቄ ነው፡፡
ከቶውኑም የውጪ ባላንጣን (external enemy) አሸንፈናል ብሎ መኩራራት፤ የውስጥ ባላንጣ (internal enemy) መፈልፈያውን ጊዜ (incubation time) እንደሚወልድ በቅጡ ማስተዋል ይገባል፡፡ የማንኛውም ሥርዓት የለውጥ ዕድገት ወይ ዝገት እንደሁኔታው የሚያጐነቁላቸው አያሌ እንግዳ-ብቃዮች ይኖራሉ፡፡ በታሪክ የታየ፣ ያለ፣ የነበረ ነው፡፡
ጉልሁንና ዋናውን ስዕል (the bigger picture) በቅጥ በቅጡ ማየቱ አግባብ የመሆኑን ያህል፤ ጥቃቅኖቹንና አንጓ ካንጓ ማያያዣዎቹን (Political ligaments) አበክሮ ማስተዋል ትልቅ ብልህነት ነው፡፡ የተጀመረው ልማት ይህን ያገናዘበ መሆን አለበት፡፡
Even lies mature ይባላል (ውሸትም እንኳን ይበስላል እንደማለት ነው፡፡) ስልክ ስንተክል፣ ኔትዎርክ ስናሰራጭ፤ መብራት ስንዘረጋ፣ ውሃ ስናስገባ፣ አጥንተንና አቅማችንን ለክተን መሆን አለበት፡፡ የልማት ስትራቴጂ ስንቀይስም አጥንተንና አቅማችንን ለክተን መሆን አለበት፡፡ አለበለዚያ “ቀድሞ ነበር እንጂ መጥኖ መደቆስ
አሁን ምን ያደርጋል ድስት ጥዶ ማልቀስ!” የሚለው ግጥም ይመጣል፡፡ በመሠረቱ ልማትን በጐ በጐውን ማየትና መኩራራት ብቻ ሳይሆን ውስጡ ያለውስ ምሥጥና ግንደ-ቆርቁር ምን ይመስላል? ብሎ፣ ይሆነኝ ብሎ ዐይንን ገልጦ ማየት የአባት ነው፡፡ እሸት እሸቱን እያየን ነቀዙን ካላስተዋልን፣ ምርቱን አይተን የግርዱን ብዛት ካላመዛዘንን፤ ሁሌ “ጉሮ-ወሸባዬ” እያልን፤ ውስጥ-ውስጡን መሽመድመዳችን አይቀሬ ይሆናል፡፡ ነገ ስለ ምርጫ ስናወራም ለህዝቡ ዕውነተኛ ገፅታችንን ማሳየት አለብን፡፡ ከልማቱ ተጠቃሚው፤ ህዝብ መሆን አለበት፤ እንጂ ከላይ ከላዩ ቦጥቧጩ መሆን የለበትም፡፡ ማርጋሬት ሚሼል “ነገም ሌላ ቀን ነው” በሚባለው መፅሀፏ ውስጥ የገለፀችው፣ ሬት በትለር የተባለው በጦርነቱ ጥቅም ያጋብስ የነበረ ነጋዴ፤ “አገር ስትለማ ቀስ በቀስ ሀብታም መሆን ይቻላል፡፡ አገር ስትጠፋ ግን በአንድ አፍታ መበልፀግ ይቻላል” የሚለን ለዚህ ነው!!