Administrator

Administrator

  ከዕለታት አንድ ቀን አንድ ይጭነው አጋሠሥ፣ ይለጉመው ፈረስ የነበረው፣ ለምድር ለሰማይ የከበደና ባለሙያ የሆነ፤ ትልቅ ጌታ፤ በአንድ አገር ይኖር ነበር፡፡
አሽከሮቹ፣ ባለሟሎቹ፣ ጋሻ- ጃግሬዎቹ ሥፍር ቁጥር የላቸውም፡፡ ከአሽከሮቹ መካከል ሁለት በጣም የሚተሳሰቡ፣ በጣም የሚግባቡ፣ ስራ ከመሥራታቸው አስቀድመው የሚመካ ኩሩ ቅንና ታታሪ አሽከሮች አሉ፡፡
አንድ ቀን አንደኛው፤ ለሁለተኛው፤
“እንደዚህ ያለ አስተዳደሪ ጌታ ስላለን ዕድለኛ እንደሆንን ይገባሃል?” ሲል ጨዋታ ያነሳል፡፡
ሁለተኛው፤
“እጅግ በጣም ዕድለኞች ለመሆናችን ምንም ጥርጥር የለኝም፡፡ እንዲያውም እስከ ዛሬ ለዋለልን ውለታ ምን ልንከፍል እንችላለን? እያልኩ ሁልጊዜ እጨነቃለሁ፤ እጠበባለሁ፡፡”
አንደኛው፤
“ዕውነትም አንድ ነገር ለማድረግ መቻል አለብን፡፡ እስቲ አንተም አስብበት፤ እኔም ላስብበትና አንድ መላ እንፈጥራለን” አለ፡፡
ሁለቱ ታማኝ አሽከሮች ለውለታው ምላሽ ምን ለማድረግ እንደሚችሉ ማሰላሰላቸውን ቀጠሉ፡፡
የሁለቱ አሽከሮች ወዳጅነት የሚያስገርመው የጎረቤት ሰው፤ አንድ ቀን ወደ ጌትዬው ይመጣና፤
“እኔ እምልህ ወዳጄ፤ አንድ ነገር ልጠይቅህ እፈልግ ነበር” አለው፡፡
ጌትዬውም፤
“ስንትና ስንት ዘመን አብረን የኖርን ጎረቤታሞች ሆነን ሳለን፤ ጥያቄህን በሆድህ ይዘህ እስከዛሬ  መቆየት የለብህም ነበር፡፡ አሁንም የፈለከውን ጠይቀኝ” አለና መለሰለት፡፡
ጎረቤትዬውም፤
“እነዚህ ሁለት ታማኝ አሽከሮችህን፤ ምን ዘዴ ተጠቅመህ ነው እንደዚህ ተዋደውና ተሳስበው እንዲያገለግሉህ ያደረግሃቸው? መቼም በዚህ አገር እንዳንተ ያለ ዕድለኛ ሰው ያለ አይመስለኝም!” አለው፡፡
ጌትዬው የመለሰው መልስ በጣም አስገራሚ ነው፡፡
“ወዳጄ! እርስ በርስ ተጣጥመው እንዲያገለግሉኝ ለማድረግ የተጠቀምኩበት ምንም ጥበብ የለም፡፡ ይልቁንም ሌት ተቀን የምጠበብ የምጨነቅበትን አንድ ነገር ልንገርህ፡-
ለእኔ የሚጠቅመኝ ከሚዋደዱ ይልቅ ቢጣሉ ነበር!”
ጎረቤትዬው በጣም ደንግጦ፤
“ለምን? እንዴት?” ሲል ጠየቀው፡፡
ይሄኔ ጌትዬው፤
“አየህ ወዳጄ! ለእኔ የሚበጀኝ ቢጣሉና አንዱ አንዱን ቢጠብቅልኝ ነበር!” አለው ይባላል፡፡
* * *
“የአልጠግብ ባይ..” አስተሳሰብ፤ ሰው ወደ ጠብ፣ ወደ ጠላትነት፣ ወደ መናቆር፣ ወደ መሰላለል፤ እንዲሄድ የሚያደርግ ነው!
ሰው ከተፋቀረ፣ ከተሳሳቀና ደስ ብሎት ካደረ ይከፋዋል፡፡ ስለዚህም እንቅልፉን አጥቶ ሲያሴር፣ ነገር ሲጠመጥም ያነጋል፡፡ ደግ እንዳይበረክት ይመኛል፡፡ መመኘት ብቻ አይደለም ጥፋት ጥፋቱን ያጎለብታል፡፡ ሰላም ይበጠብጠዋል፡፡ የማሪያም መንገድ ሲታይ ዐይኑ ይቀላል! ወገን ከወገኑ ሲለያይ፣ ዘር ከዘር ሲደማማ፣ ሲቋሰል፤ ህልውና ይረጋገጥለት ይመስለዋል፡፡ እየዘረፈ፣ እየመዘበረ የገነባው ፎቅ ውሎ አድሮ ይነካበት አይመስለውም፡፡ የድሀ ዕንባ ጎርፍ ሆኖ ይወስደው አይመስለውም፡፡ ዘላለም እያባላሁ፣ እያናከስኩ እኖራለሁ፤ ይላል! እንደ ሁልጊዜው፤ ረዥም ጊዜ መኖርን ከዘለዓለማዊነት ጋር ያምታታዋል (He mistakes longevity for eternity)፡፡ የማታ ማታ ግን ተመናምኖ ተበትኖ ያበቃል! ይህ በታሪክ የታየ፣ ነገም የሚታይ ገሀድ ዕውነት ነው፡፡ “ሞት ቢዘገይ የቀረ ይመስላል” ነው ጉዳዩ!
አንድ፤ ጃንሆይ (ቀዳማይ ኃይለ ሥላሴ) ተናገሩት የሚባል መሠረታዊ አባባል አለ፡፡ አቃቤ- ሰዓት ተሰጥቶት ጉዳዩን በቅጥፈት ላስረዳቸው ሚኒስትር ያሉት ነገር ነው ይባላል፡-
“…ያልተሠራውን ሠርቻለሁ እያሉ መደለልና ወደፊትም እሠራለሁ እየተባለ ሐሳብን በሸምበቆ መሠረት ላይ መገንባት፣ ታላቅ ጉዳት የሚያስከትል ስለሆነ፤ የሠራኸውንም ሆነ ወደፊት ለመሥራት የምታስበውን እየለየህ በጥልቀት አጥናው…”
ይህ ዛሬም ላገራችን ባለሥልጣኖች የሚሠራ መሆኑን ልብ እንበል!
ሀገራችን ወደፊት ትራመድ ዘንድ የተደቀኑባትን አንዳንድ ጥያቄዎች በጥንቃቄ መመለስ ይገባታል፡፡
እነዚህ ጥያቄዎች በመሪዎች ጫንቃ ላይ ብቻ የምንጭናቸው ሳይሆኑ የሁላችንንም እርዳ-ተራዳ የሚሹ ናቸው፡፡ ተነጣጥለን የምንታገልባቸው ሳይሆኑ አንድነታችንን ልንፈትሽባቸው ግድ የሚሉ ናቸው፡፡ እነሆ፡-
ምን ዓይነት ዲሞክራሲ እንዲኖረን እንፈልጋለን? ቀጣዩን ሥርዓት ለመገንባት የእስካሁኑን በምን መልክ ብንገላገለው፣ ብንጠግነው ወይም ብናድሰው ይሻላል? ህገ-መንግስቱ ላይ ያየናቸው እንከኖች የቶቹ ናቸው? ምን ቢደረጉ ይመረጣል? ዕውን የሽግግር መንግሥት ያስፈልጋል? በኢትዮ-ኤርትሪያ ዙሪያ የተጀመረው መልካም ጉርበትና እንዴት ይቀጥል? በዝርዝር ጉዳዩን ማን ያውጠንጥን? ቀድሞ በ1983 ዓ.ም ከምናውቀው ግንኙነታችን የተለየ ምን መልክ ይያዝ? ኮንፌዴሬሽን አዋጭ አካሄድ ነው ወይ? የህወኃት እና የአዲሱ ጠ/ሚኒትር አቅጣጫ ግንኙነት ውስጥ የኢትዮጵያ ህዝብ ሚና ምን መሆን አለበት? ከህገ መንግሥት ማሻሻልና ከምርጫው የቱ ይቅደም? ለመሆኑ ፕራይቬታይዤሽን ያዋጣል? የምሥራቅ አፍሪካን መሪነት ማን ይይዛል? ያልተረጋጋውና የማይረጋጋው (ever volatile) የአፍሪካ ቀንድ ዕጣ-ፈንታ ምን ይሆን? በኢትዮጵያ ጉዳይ ዕውነተኛ ህዝበ- ተሳትፎ እንዴት ለማምጣት ይቻላል? ኢህአዴግ ከግንባር ወደ ውህደት ሊመጣ ይቻለዋልን? ህወኃት እና የትግራይ ህዝብ እንዴት ይታያሉ? ዕውነት ህወኃት የመሰነጣጠቅ አደጋ ላይ ነው? የግለሰቦች ብቻ ሳይሆን ተቋማዊ የሆነን ጥንካሬ እንደምን ማምጣት ይቻላል? ሙስና በማስፈራራት ይቆማል? እስካሁን የወጡ ህጎች የፕሬስ፣ የፀረ ሽብር፣ የብሮድካስት ወዘተ እንዴት ይሻሻሉ? ያለው መንግሥት የህዝብ አመፅ የወለደው ነው? አለመረጋጋቱ ተገቷል ወይስ ሊቀጥል ይችላል?...
ጥያቄዎቻችን በርካታ ናቸው፡፡ የሚመለከተው አካል በአግባቡ ሊመልሳቸው ይገባል፡፡ ከእንግዲህ ማድበስበሱም ሆነ ቆይ-ነገ- ማለቱ (Procrastination) ለማንም አይጠቅምም፡፡ ሳንፈታቸው መጓዝና እርምጃ አለመውሰድ ስህተት ነው!! ይህን ስህተት ደግመን ከሠራን “ትላንት ማታ ቤትህ ስትገባ የመታህ የድንጋይ እንቅፋት ዛሬም ከደገመህ፤ ድንጋዩ አንተ ነህ” የሚለው የቻይናዎች አባባል እኛ ላይ ሠራ ማለት ነው፡፡ ሰብሰብ፣ ጠንቀቅና ጠበቅ እንበል! ሁሉንም ደበላልቀን አንድ ላይ ከመፍጨት፣ በየከረጢቱ አስቀምጠን መቋጠር በመልክ በመልኩ ለመፍት ያመቻል፡፡ (From smashed potato to potato-sacks እንደሚሉት መሆኑ ነው)

የብአዴን ማዕከላዊ ኮሚቴ ሃላፊ እና የአማራ ክልል ፕሬዚዳንት የህዝብ ግንኙነት አደረጃጀት አማካሪ የነበሩት አቶ ተስፋዬ ጌታቸው ከዚህ አለም በሞት ተለይተዋል፡፡
አቶ ተስፋዬ ጌታቸው የአማራ ክልል የገበያ፣ ንግድና ኢንዱስትሪ ልማት ቢሮ ሃላፊ ሆነው የሠሩ ሲሆን የብአዴን ማዕከላዊ ኮሚቴ ፅ/ቤት ሃላፊ ሆነው ከተሾሙ ጥቂት ወራትን ብቻ ነበር ያስቆጠሩት፡፡
በአሜሪካን ሃገር በህክምና ላይ ሣሉ ህይወታቸው ያለፈው አቶ ተስፋዬ፤ በተለይ በኢትዮጵያ ውስጥ እየተካሄደ ያለውን የለውጥ እንቅስቃሴ በብርቱ ይደግፉ ከነበሩ አመራሮች ተጠቃሽ እንደነበር ታውቋል፡፡


ከተለያዩ የአለማችን አገራት ወደ ኢትዮጵያ ከሚገቡት የተለያዩ ከባድና ቀላል ተሽከርካሪዎች መካከል 85 በመቶ ያህሉ በውጭ አገራት ለ20 አመታትና ከዚያ በላይ አገልግሎት የሰጡ መሆናቸውን አንድ አለማቀፍ ሪፖርት አስታውቋል፡፡
ሴንተር ፎር ሳይንስ ኤንድ ኢንቫይሮመንት የተሰኘው ተቋም ባለፈው ማክሰኞ ይፋ ባደረገው አለማቀፍ የጥናት ሪፖርት እንዳለው፣ በአሁኑ ወቅት በመላ አገሪቱ አገልግሎት በመስጠት ላይ ከሚገኙ ተሽከርካሪዎች መካከል አብዛኞቹ 30 አመታትና ከዚያ በላይ ያገለገሉ ናቸው ተብሎ ይገመታል፡፡
በኢትዮጵያ አገልግሎት የሚሰጡ የከባድና ቀላል ተሽከርካሪዎች ቁጥር ባለፉት 15 አመታት በስድስት እጥፍ ያህል ማደጉን የጠቆመው ሪፖርቱ፣ ከተመረቱ ረጅም ጊዜ ያስቆጠሩ ተሽከርካሪዎች ከውጭ አገራት እንዳይገቡ የሚከልክል የዕድሜ ገደብ ህግና መመሪያ አለመኖሩንና ለረጅም ጊዜ አገልግሎት የሰጡ በርካታ ተሽከርካሪዎች ወደ አገሪቱ እንደሚገቡ አመልክቷል፡፡
በርካታ የአፍሪካ አገራት ለረጅም ጊዜ አገልግሎት የሰጡ አሮጌ መኪኖችን ካደጉት አገራት በከፍተኛ መጠን እንደሚያስገቡ የጠቆመው የተቋሙ ሪፖርት፣ ይህም የአገራቱን ዜጎች ከአካባቢ ብክለት ጋር ተያይዘው ለሚከሰቱ የጤና ችግሮችና ለመኪና አደጋዎች እየዳረገ እንደሚገኝ አመልክቷል፡፡

Saturday, 21 July 2018 14:08

ሰሞነኛ ወሬዎች

 የአዲስ አበባ ቀላል ባቡር ሠራተኞች አድማ

የአዲስ አበባ ቀላል ባቡር ሠራተኞች፤ ደሞዝና ጥቅማጥቅም አነሰን በሚል በሳምንቱ መጀመሪያ ላይ ለሁለት ቀናት የሥራ ማቆም አድማ አደረጉ፡፡
በጥቅማጥቅም ጉዳይ ከምድር ባቡር አስተዳደር ጋር የተስማሙ ሲሆን በደሞዝ ጉዳይ ግን ለወደፊት እንስማማለን ብለው ከሁለት ቀናት አድማ በኋላ ሐሙስ እለት ስራቸውን ጀምረዋል። በሥራ ማቆም አድማው ምድር ባቡር 1 ሚሊዮን ብር ያህል ሳያጣ እንዳልቀረ ይገመታል፡፡

     አዲስ አበባ አዲስ ከንቲባ አግኝታለች

የአዲስ አበባ አስተዳደር ከንቲባ ሆነው ለ5 ዓመታት ያገለገሉት አቶ ድሪባ ኩማ ከስልጣን ተነስተው የካናዳ አምባሣደር ሆነው መሾማቸውን ተከትሎ፣ አዲስ አበባ የምክር ቤቷ አባል ባልሆኑት ኢንጂነር ታከለ ኡማ እንድትመራ ተወስኗል፡፡
ኢንጂነር ታከለ ኩማ የቀድሞ የሰበታ ከተማ ከንቲባ ሲሆኑ አዲስ አበባን በምክትል ከንቲባነት ያስተዳድራሉ፡፡ ወ/ሮ ዳግማዊት ሞገስ እና ዶ/ር ሠለሞን ም/ከንቲባዎች ሆነዋል፡፡

        እንባ ያራጨው የመጀመሪያው የአስመራ በረራ
 
ኤርትራና ኢትዮጵያ በይፋ እርቅ ማውረዳቸውን ተከትሎ የኢትዮጵያ አየር መንገድ ባለፈው ረቡዕ 460 ተጓዦችን ከአዲስ አበባ አሳፍሮ ወደ አሥመራ የበረረ ሲሆን በዚህ ከ20 ዓመት በኋላ ለመጀመሪያ ጊዜ በተደረገ ታሪካዊ በረራ፤ ለዓመታት የተቆራረጡና የተነፋፈቁ ቤተሰቦች በእንባ እየተራጩ ናፍቆታቸውን ተወጥተዋል፡፡
“ይህ የተፈጠረው ሰላም በጣም ያስደስታል፤ ከሰማይ የመጣ ነው የሚመስለው” ብሏል፤ ከ20 ዓመት በኋላ ከቤተሰቦቹ ጋር የተገናኘ ኤርትራዊ ወጣት፡፡
ይህን የጉዞ ቡድንም የቀድሞ ጠቅላይ ሚኒስትር አቶ ሃይለማርያም ደሣለኝ እና ባለቤታቸው ወ/ሮ ሮማን ተስፋዬ መርተውታል፡፡

    የደህንነት ሰራተኞች የፓርቲ አባል መሆን አይችሉም

የብሄራዊ መረጃ እና ደህንነት አገልግሎት አዲሱ ሃላፊ ጀነራል አደም መሃመድ፤ የደህንነት ባለሙያዎች የፖለቲካ ፓርቲ አባል መሆን እንደማይችሉ ገለጹ፡፡
የተቋሙ ሃላፊዎች ሰሞኑን ከሰራተኞች ጋር ባደረጉት ስብሰባ፤ ”የማንኛውም የፖለቲካ ፓርቲ አባል የሆናችሁ ወይ ተቋሙን አሊያም ፓርቲውን ልቀቁ” ብለዋል፤ ጀነራል አደም፡፡ ጠ/ሚኒስትር ዶ/ር ዐቢይ አህመድ፤ በመከላከያ ሚኒስቴርና በደህንነት ተቋም ላይ የሪፎርም ሥራ መጀመሩን መናገራቸው አይዘነጋም፡፡

    ቴዲ አፍሮ በአዲስ አበባ  ኮንሰርት ያቀርባል

ድምጻዊ ቴዎድሮስ ካሣሁን (ቴዲ አፍሮ) በሚሊኒየም አዳራሽና በመስቀል አደባባይ ኮንሠርት ያቀርባል፡፡ ኮንሠርቶቹ መቼ እንደሚቀርቡ ባይገለፅም ለአዲስ ዓመት ወይም ለመስቀል ሊሆን እንደሚችል ተገምቷል፡፡
በሚሊኒየም አዳራሽ የሚቀርበው ኮንሰርት ከፍ ያለ የመግቢያ ክፍያ የሚኖረው ሲሆን በመስቀል አደባባይ የሚዘጋጀው የሙዚቃ ድግስ ግን በነፃ እንደሚሆን ታውቋል፡፡

      የተቃውሞ ሰልፍ በመቐሌ

ከተለያዩ የሃገሪቱ ክፍሎች በግፍ ተፈናቅለናል የሚሉ በ10 ሺዎች የሚቆጠሩ ዜጎች በመቐሌ የሠማዕታት ሃውልት ፊት ለፊት ከትናንት በስቲያ ተቃውሞ አሰምተዋል፡፡
ያለ ምንም ጠያቂ አውላላ ሜዳ ላይ ወድቀናል ያሉት ተጎጂዎቹ፤ ለክልሉ መንግስት በተደጋጋሚ አቤት ብንልም ምላሽ ማግኘት አልቻልንም ሲሉ ምሬታቸውን ገልጸዋል።
ተቃዋሚዎቹ የክልሉ ምክትል ርዕሰ መስተዳደር ዶ/ር ደብረፅዮን ገ/ሚካኤል መጥተው የማያነጋግሩን ከሆነ ከሰልፋችን ንቅንቅ አንልም ብለው እንደነበርና በኋላ ግን በፀጥታ አካላት የማረጋጋት ሥራ መበተናቸውን ለማወቅ ተችሏል።  

      ኢትዮ-ቴሌኮም አዲስ ሥራ አስፈጻሚ ተሾመለት

የኢትዮ-ቴሌኮም ስራ አስፈጻሚ በመሆን ድርጅቱን ለ3 ዓመት የመሩት ዶ/ር አንዷለም አድማሴ፤ ከሃላፊነታቸው ተነስተው ምክትላቸው ወ/ሮ ፍሬህይወት ታምሩ በሥራ አስፈጻሚነት ተሾመዋል፡፡
ኢትዮ ቴሌኮም በከፊል ወደ ግል ይዞታነት እንዲዘዋወሩ ከተወሰነባቸው የመንግስት የልማት ድርጅቶች አንዱ ነው፡፡ ዶ/ር አንዷለም አድማሴ፤ የከፍተኛ ትምህርት ጥራት ድርጅት ዋና ዳይሬክተር ሆነው ተመድበዋል፡፡

 ጎግል የ5 ቢሊዮን ዶላር ቅጣት ተጣለበት


    ታዋቂው የማህበራዊ ድረገጽ ትዊተር በግንቦትና በሰኔ ወር ብቻ ህገወጥ ድርጊት የሚፈጽሙና የተጭበረበሩ ያላቸውን የ70 ሚሊዮን ያህል ተጠቃሚዎቹን አካውንቶች በመዝጋት አገልግሎቱን እንዳያገኙ ማድረጉን ዋሽንግተን ፖስት ዘግቧል፡፡
የተጭበረበሩና ህገወጥ ድርጊቶችን በሚፈጽሙ ተጠቃሚዎቹ ላይ የሚያደርገውን ቁጥጥርና የሚወስዳቸውን እርምጃዎች እያጠናከረ የመጣው ትዊተር፤ የተጠቃሚዎቹን ቁጥር በከፍተኛ ሁኔታ የመቀነስ እርምጃው ገቢውንና ትርፋማነቱን አደጋ ውስጥ እንዳይከተው መሰጋቱን ዘገባው አመልክቷል፡፡
እ.ኤ.አ በ2016 ከተካሄደው የአሜሪካ ፕሬዚዳንታዊ ምርጫ ቅስቀሳ ጋር በተያያዘ ተጠቃሚዎች ያልተገባ ድርጊት መፈጸማቸውን ተከትሎ  የተጭበረበሩ አካውንቶችን በመጠቀም የተሳሳቱ መረጃዎችንና አደገኛ መልዕክቶችን በሚያሰራጩ ተጠቃሚዎች ላይ የሚወስደውን እርምጃ ያጠበቀው ትዊተር፤ ባለፈው የፈረንጆች አመት 2017 የመጨረሻዎቹ አራት ወራት ጊዜ ውስጥ ብቻ የ58 ሚሊዮን ተጠቃሚዎቹን አካውንቶች መዝጋቱን የዘገበው ደግሞ አሶሼትድ ፕሬስ ነው፡፡
በተያያዘ ዜናም፣ የአውሮፓ ህብረት የንግድ ውድድርንና የሞባይል ተጠቃሚ ደንበኞችን ምርጫ የሚገድብ ህገወጥ ድርጊት ፈጽሟል በሚል ባለፈው ረቡዕ በታዋቂው የአሜሪካ ኩባንያ ጎግል ላይ ክብረወሰን የተመዘገበበትን የ5 ቢሊዮን ዶላር ቅጣት ማስተላለፉ ተዘግቧል፡፡
ጎግል የራሱ ምርት የሆነውን አንድሮይድ ኦፐሬቲንግ ሲስተም የሚጠቀሙ የሞባይል ስልኮችን የሚያመርቱ ኩባንያዎችን፣ የራሱ ምርት የሆኑ ሌሎች የፍለጋ አፕሊኬሽኖችን ኢንስቶል እንዲያደርጉ አስገድዷል በሚል ከአውሮፓ ህብረት የተላለፈበትን የገንዘብ ቅጣት ውሳኔ እንደማይቀበልና ይግባኝ እንደሚጠይቅ አስታውሷል፡፡
የአውሮፓ ህብረት ከሶስት አመታት ምርመራ በኋላ በጎግል ላይ ያስተላለፈው ይህ የገንዘብ ቅጣት፣ በታሪኩ ከንግድ ውድድር ህጎች ጥሰት ጋር በተያያዘ በአንድ ኩባንያ ላይ የጣለው ከፍተኛው ገንዘብ እንደሆነም አሶሼትድ ፕሬስ ዘግቧል፡፡

 በ50 የተለያዩ የዓለማችን አገራት የኤችአይቪ ኤድስ ስርጭት እየጨመረ መምጣቱንና በቫይረሱ እየተጠቁ ካሉት ሰዎች ግማሽ ያህሉ የመድሃኒትና የህክምና አገልግሎቶችን እያገኙ እንዳልሆነ ዩኤንኤድስ የተባለው አለማቀፍ ተቋም ባወጣው ሪፖርት አስታውቋል፡፡
የኤችአይቪ ቫይረስን ስርጭት ለመግታት በአለማቀፍ ደረጃ እየተከናወኑ ያሉ ተግባራት እየተዳከሙ መሆናቸውን የጠቆመው የተቋሙ ሪፖርት፤ በ50 ያህል የአለማችን አገራት የቫይረሱ ስርጭት ጭማሪ ማሳየቱም ለጉዳዩ የሚሰጠው ትኩረት አናሳ እየሆነ መምጣቱን እንደሚያመላክት ገልጧል፡፡
የቫይረሱ ስርጭት በአንዳንድ አገራት ጥሩ በሚባል ሁኔታ መቀነስ ማሳየቱን የጠቆመው ዘገባው፤ በአለማችን በቫይረሱ የሚያዙ ሰዎች ቁጥር በከፍተኛ ሁኔታ የቀነሰው ከዚህ በፊት በቫይረሱ ክፉኛ በተጠቁት የምስራቅና ደቡባዊ አፍሪካ አገራት ሲሆን፣ ለዚህ መሻሻል በምክንያትነት የጠቀሰውም የህብረተሰቡ ግንዛቤ በጥሩ ሁኔታ ማደጉና አብዛኞቹ የቫይረሱ ተጠቂዎች የኤችአይቪ ህክምና በአግባቡ ማግኘታቸው መሆኑን አስረድቷል፡፡
በምዕራብና በመካከላዊ አፍሪካ አገራት የኤችአይቪ ህክምና አገልግሎት ማግኘት የሚገባቸው በርካታ ዜጎች የአገልግሎቶች ተጠቃሚ አይደሉም ያለው ሪፖርቱ፤ በአገራቱ 75 በመቶ ህጻናት እና 60 በመቶ አዋቂዎች የሚገባቸውን የኤችአይቪ ህክምና እንዳላገኙም ጠቁሟል፡፡   
በአሁኑ ወቅት በመላው አለም በኤችአይቪ ቫይረስ የተጠቁ 37 ሚሊዮን ያህል ሰዎች መኖራቸውን የዘገበው ቢቢሲ በበኩሉ፣ በአለማችን የተለያዩ አገራት በየአመቱ አንድ ሚሊዮን ያህል ሰዎች በቫይረሱ ሳቢያ ለህልፈተ ህይወት እንደሚዳረጉም አመልክቷል፡፡

 - 9 ሚሊዮን አፍሪካውያን በከፋ ባርነት ውስጥ ይኖራሉ
  - በአለማችን ባለፉት 19 ወራት 40ሚ. ሰዎች የባርነት ሰለባ ሆነዋል

    ሰሜን ኮርያና ኤርትራ በርካታ ዜጎች ለዘመናዊ ባርነት ተዳርገው የሚኖሩባቸው ቀዳሚዎቹ የአለማችን አገራት መሆናቸውንና ባለፉት 2 አመታት በመላው አለም ከ40 ሚሊዮን በላይ የተለያዩ አገራት ዜጎች የዘመናዊ ባርነት ሰለባዎች መሆናቸውን ዎክ ፍሪ ፋውንዴሽን የተባለው አለማቀፍ የሰብዓዊ መብቶች ተሟጋች ተቋም አስታውቋል፡፡
ተቋሙ ከትናንት በስቲያ ይፋ ባደረገው የ2018 የፈረንጆች አመት አለማቀፍ የባርነት ደረጃ ሁኔታ አመላካች ሪፖርት፣ ሰሜን ኮርያ በቀዳሚነት የተቀመጠች ሲሆን ከአገሪቱ አጠቃላይ ህዝብ 10 በመቶ የሚሆነው የዘመናዊ ባርነት ሰለባ መሆኑን አስታውቋል፡፡ በአመቱ የተቋሙ ሪፖርት ከአለማችን አገራት ሁለተኛ ደረጃን በያዘቺው ኤርትራም፣ በርካታ ቁጥር ያላቸው ዜጎች በብሔራዊ ውትድርና ግዳጅና በሌሎች የጉልበት ብዝበዛዎች ለአስርት አመታት የከፋ የባርነት ኑሮን ሲገፉ ኖረዋል መባሉን የዘገበው ሮይተርስ፤ በሪፖርቱ ሶስተኛ ደረጃን የያዘቺው ብሩንዲ መሆኗንም ጠቁሟል፡፡
በሶስቱም አገራት መንግስታት ዜጎቻቸውን ለጉልበት ብዝበዛና ለሌሎች የዘመናዊ ባርነት ጭቆናዎችና ድርጊቶች እየዳረጉ እንደሚገኙ የጠቆመው የሮይተርስ ዘገባ፤ በመላው አፍሪካ ከ9 ሚሊዮን በላይ አፍሪካውያን አስከፊ የባርነት ኑሮን በመግፋት ላይ እንደሚገኙም በሪፖርቱ መጠቀሱንም አመልክቷል፡፡
በተለያዩ አለማችን አገራት የሚከሰቱ ግጭቶችና የአገራት መንግስታት የሚያሳድሩት ጭቆና በርካታ ቁጥር ያላቸውን ዜጎች ለከፋ ዘመናዊ ባርነት መዳረጋቸውን የጠቆመው ሪፖርቱ፤ ዘመናዊ ባርነት ተስፋፍቶባቸዋል በሚል ከጠቀሳቸው ሌሎች አገራትም ውስጥ መካከላዊ አፍሪካ ሪፐብሊክ፣ አፍጋኒስታን፣ ደቡብ ሱዳንና ፓኪስታን ይገኙበታል፡፡
እ.ኤ.አ ከ2016 አንስቶ ባለው ጊዜ ውስጥ በመላው አለም ከ40 ሚሊዮን በላይ የተለያዩ አገራት ዜጎች የዘመናዊ ባርነት ሰለባዎች ሆነዋል ሲሉ ዎክ ፍሪ ፋውንዴሽንና አለማቀፉ የስራ ድርጅት ማስታወቃቸውን የዘገበው ሮይተርስ፤ ተቋሙ እ.ኤ.አ በ2016 ይፋ ባደረገው ሪፖርቱ ከአለማችን አገራት መካከል በርካታ ቁጥር ያላቸው ዜጎች የዘመናዊ ባርነት ሰለባዎች የሆኑባት ቀዳሚዋ አገር ህንድ እንደነበረችና በአመቱ 18.4 ሚሊዮን ያህል ህንዳውያን የዘመናዊ ባርነት ሰለቦች እንደነበሩም አስታውሷል፡፡

  የጸረ-አፓርታይድ ታጋዩና የቀድሞው የደቡብ አፍሪካ ፕሬዚዳንት ኔልሰን ማንዴላ 100ኛ ዓመት የልደት በአል ባለፈው ረቡዕ በደቡብ አፍሪካና በሌሎች አገራት በተለያዩ ዝግጅቶች መከበሩን ቢቢሲ ዘግቧል፡፡
ደቡብ አፍሪካውያን ከአምስት አመታት በፊት ከዚህ አለም በሞት የተለዩትን ኔልሰን ማንዴላን መልካም ስራዎችና አፓርታይድን በመታገል ያበረከቱትን ታሪካዊ አስተዋጽኦ በመዘከርና የበጎ አድራጎት ስራዎችን በማከናወን የ100ኛ ዓመት የልደት በአላቸውን ማክበራቸው ተነግሯል፡፡
ያም ሆኖ ግን፣ ጥቂት ደቡብ አፍሪካውያን ማንዴላ የታገሉለት የቀለም ልዩነትና ኢ-ፍትሃዊ የሆነ የሃብት ክፍፍል ለዘመናት ተሻግሮ አሁንም ድረስ ስር ሰድዷል በሚል የማንዴላን ስኬት ጥያቄ ውስጥ መክተታቸውንና የልደት በአሉ በመከበሩ ደስተኞች አለመሆናቸውን ሲገልጹ መደመጣቸውን ዘገባው አመልክቷል፡፡
የቀድሞው የአሜሪካ ፕሬዚዳንት ባራክ ኦባማ፤የማንዴላን የልደት በዓል ምክንያት በማድረግ ከ44 የተለያዩ አገራት ለተውጣጡና በኦባማ ፋውንዴሽን የአፍሪካ ሊደርሺፕ ፕሮግራም ለታቀፉ 200 ወጣት አፍሪካውያን መሪዎች በጆሃንስበርግ አነቃቂና የማንዴላን ታላቅነት የሚዘክር ንግግር ማድረጋቸውንም ዘገባው አመልክቷል፡፡


              ከአዲስ አበባ ከ800 በላይ ሰው ይጓዛል
            በጉራጌ ልማትና ባህል ማህበር አስተባባሪነት ዛሬ ለስድስተኛ ጊዜ በሚካሄደው የችግኝ ተከላ ዘመቻ፣ በጉራጌ ዞን በ13ቱም ወረዳዎች ከ8 ሚ. በላይ ችግኞች እንደሚተከሉ የጉራጌ ልማትና ባህል ማህበር አስታወቀ፡፡ በችግኝ ተከላው ከ1 ሺህ ሰዎች በላይ የሚሳተፉ ሲሆን ከአዲስ አበባ ብቻ ከ800 በላይ ሰው ወደ ስፍራው እንደሚያቀና የማህበሩ የህዝብ ግንኙነት ኃላፊ አቶ መንግስቱ ኃይለማሪያም ተናግረዋል፡፡
ማኅበሩ ላለፉት አምስት ዓመታት ያለማቋረጥ በጉራጌ ዞን ወረዳዎች በርካታ ችግኞችን ከመትከሉም በላይ መፅደቃቸውን በማረጋገጥና በመንከባከብ በኩልም ውጤታማ ስራ መሥራቱን ኃላፊው ባለፈው ሳምንት መጀመሪያ በማህበሩ ጽ/ቤት በሰጡት ጋዜጣዊ መግለጫ አስታውቀው፣ ለችግኝ ተከላው የሚያስፈልገውን ከአንድ ሚ. ብር በላይ ከአካባቢው ተወላጅ ባለሀብቶችና ከተለያዩ ድርጅቶች መሰብሰብ መቻሉን ገልፀዋል፡፡
ከአዲስ አበባ ሚኒስትሮች፣ ሚኒስትር ዴኤታዎች፣ የተለያዩ ቢሮ ኃላፊዎች፣ የፓርላማ አባላት፣ ባለሀብቶች፣ የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ኃላፊዎች ከክፍለ ከተሞችና ከወረዳዎች፣ እንዲሁም የተለያዩ የህብረተሰብ ተወካዮችና ታዋቂ ግለሰቦች በዛሬው የችግኝ ተከላ ላይ ይሳተፋሉ ተብሎ እንደሚጠበቅና ለጉዞውም ከ14 በላይ አውቶብሶች መዘጋጀታቸውን አቶ መንግስቱ ኃ/ማርያም ጨምረው ገልፀዋል፡፡
የጉራጌ ልማትና ባህል ማዕከል፤ በጤና፣ በትምህርት በባህል ማበልፀግና በተለያዩ ዘርፎች የልማት ስራዎችን በመስራት የሚታወቅ ሲሆን በተጨማሪም ከደን ምንጣሮና ከአካባቢ መራቆት፣ ከጊዜ ወደ ጊዜ እየተባባሰ የመጣውን የአየር ንብረት ለውጥ ለመቋቋምና አካባቢውን ጤናማ ለማድረግ ወደ ችግኝ ተከላ ፊቱን በማዞር፣ ውጤታማ ስራ መስራት መቻሉንና ይሄው ተግባር በየዓመቱ ተጠናክሮ እንደሚቀጥል ኃላፊው አስታውቀዋል፡፡

Saturday, 21 July 2018 13:05

ወንዶችና የጡት ካንሰር…

  ….አንድ ስራ ልቀጠር አስቤ በቅድሚያ የጤና ምርመራ ማቅረብ ስለነበረብኝ ወደ ሕክምና ባለሙያ ዘንድ ቀረብኩ። እሱም …የሚሻለው ወደ ግል ሐኪምህ ሄደህ ብትታይ ጥሩ ነው …አለኝ፡፡ ወደሁዋላ መለስ ብዬ ሳስበው…ላለፉት ሁለት አመታት አንድ ችግር ገጥሞኝ ነበር፡፡ በሰውነቴ ላይ በተለይም በጡቴ አካባቢ አንድ ትክክል ያልሆነ ተፈጥሮአዊ ቅርጽ ማየት ጀመርኩ፡፡ ለካስ የጡት ካንሰር የሚባል በሽታ ቀስ በቀስ እየተስፋፋ ኖሮአል፡፡ እኔ የነበረኝን ስሜት ችላ ብዬ ነበር የቆየሁት። አሁን ግን ሕይወቴ አደጋ ላይ ነው፡፡
አንድ ምክር አለኝ፡፡ እባካችሁ ማንኛችሁም ብትሆኑ ትንሽ ነገር ነው ብላችሁ ችላ አትበሉ፡፡ ምንም አዲስ ነገር ቢሰማችሁ በፍጥነት ወደባለሙያዎች በመቅረብ ምንነቱን ተረዱ፡፡
ጽሁፉን ያገኘንበት ምንጭ ያሰፈረው የግለሰብ ታሪክ ነው፡፡
የጡትን ተፈጥሮ ስንመለከት ወንዶችም ሴቶችም ከተፈጥሮ የሰውነት አካላቸው መካከል ጡት የሚባል ነገር መኖሩ እሙን ነው፡፡ የሴቶች ጡት በተፈጥሮአቸው ባላቸው ሆርሞን ሳቢያ እንዲያድግና የተለያዩ ተፈጥሮአዊ ግዴታዎችን እንዲወጣ የሚያስችል ይሆናል፡፡ የወንዶች ጡት ግን በደረት ላይ ተፈጥሮውን ለማመላከት ያህል ይታያል እንጂ ወደየትም የማያድግ እና ምንም የተለየ አገልግሎት ማለትም ለልጆች እንደወተት መስጠት የመሳሰሉትን ግዴታዎች እንዲወጣ የማይጠበቅ ነው። በእርግጥ ሴቶች ጡታቸው ወተት የሚያመርተው ከእርግዝና ጋር በተያያዘ በሚኖር ተፈጥሮአዊ ሂደት ነው፡፡
የጡት ካንሰር ለወንዶች አልፎ አልፎ የሚከሰት ሕመም እንጂ እንደሴቶቹ በስፋት የሚስ ተዋል አይደለም። ምናልባትም ከሚከሰቱት የጡት ካንሰር ሕመሞች ከ1% በታች የሚሆነው በወንዶች ላይ የሚከሰት ይሆናል፡፡ ወንዶች በሕይወት ዘመናቸው በጡት ካንሰር ሕመም የሚ ጠቁት ከ1000/ከአንድ ሺህዎቹ አንድ ሰው ቢሆን ነው፡፡ ይሄ ሲታይ ምናልባትም ወንዶች የጡት ካንሰር ሕመም አይይዛቸውም ለማለት ሊያስደፍር ይችል ይሆናል፡፡ ነገር ግን እውነታው በመጠኑም ቢሆን ወንዶች ጡታቸውን ሊታመሙ ይችላሉ፡፡
ወንዶች የጡት ካንሰር ይዞአቸዋል የሚያሰኙ አንዳንድ ምልክቶች አሉ፡፡
በጡት ላይ የመጠጠር ወይንም የማበጥ ምልክት ይታያል፡፡ በእርግጥ ካልነኩት በስተቀር ሕመም ላይሰማ ይችላል፡፡
የጡት መደደር መኖሩ የማይታወቅ እና በራሱ ጊዜ በጡት ውስጥ ወዲያ ወዲህ የማይንቀሳቀስ ነው፡፡
የጡት ጫፍ አቅጣጫ ጠመም የማለት ነገር ሊታይበት ይችላል፡፡
ከጡት ጫፍ ፈሳሽ የመውጣት ነገር ይስተዋላል፡፡አንዳዴም የደም ምልክት ሊታይበት ይችላል፡፡
በጡት ጫፍ ዙሪያ ምቾት የማይሰጥ የህመም ስሜት ሊኖር ይችላል፡፡
የጡት ጫፍ ወይም በዚያ አካባቢ ባለው ቆዳ ላይ የመቅላት የመደደር ወይንም የማበጥ ሁኔታ ይስተዋላል፡፡
ወንዶች ብዙ ጊዜ ይህ ህመም ይደርስብኛል ብሎ ካለማሰብ ነገሩን ችላ የማለት ነገር ይስተዋ ልባቸዋል። በእርግጥ ሁኔታው እንደሴቶቹ በተስፋፋ መልኩ የሚያጋጥም ባይሆንም እንደችግር ግን መስተዋሉ አይቀርም፡፡  
ለጡት ካንሰር ወንዶች ሊጋለጡ የሚችሉባቸው የተለያዩ ምክንያቶች አሉ፡፡
እድሜ፤ ይህ በምክንያትነት ከሚጠቀሱት ውስጥ ከፍተኛውን ድርሻ የሚይዘው ነው፡፡ ልክ ሴቶች   በእድሜ ምክንያት ለጡት ካንሰር እንደሚጋለጡት ሁሉ ወንዶችም ይጋለጣሉ። ወንዶች በእድ ሜያቸው ወደ 68/አመት ሲሆናቸው ለጡት ካንሰር የመጋለጥ እድል ሊያጋጥማቸው ይችላል፡፡ ከፍተኛ የኢስትሮጂን መጠን፤ በጡት አካባቢ ያሉ ሴሎች እድገት በትክክለኛውም ወይንም ትክክል ባልሆነው መንገድ የሚከሰት ሲሆን ኢስትሮጂን እንዲኖር ያደርጋል፡፡ ወንዶች በከፍተኛ ደረጃ ይህ ኢስትሮጂን ሊያጋጥማቸው የሚችለው፤ የሆርሞን መድሀኒቶችን ከመውሰድ፤ ከልክ ያለፈ ክብደት ሲኖር፤ እና የኢስትሮጂን መመረትን የሚጨምር ሲሆን ነው፡፡
በአኑዋኑዋር ምክንያት ለኢስትሮጂን መጋለጥ ፤ የአልኮሆል መጠጦች ሱሰኛ መሆን፤ እና በዚህም የተነሳ ጉበት በደም ውስጥ ሊኖር የሚገባውን ኢስትሮጂን መመጠን ሲያቅተው፤ የጉበት በሽታ ሲኖር እና በዚህም ሳቢያ አንድሮጂን(የወን ዶችን ሆርሞን) ዝቅ ሲያደርገው እንዲሁም ኢስትሮጂንን ማለትም (የሴቶችን ሆርሞን )ከፍ ሲያደርገው ችግሩ ሊከሰት ይችላል፡፡:
ከቤተሰብ ጋር በተያያዘ ፤ ይህ የጡት ካንሰር ሕመም የነበረና ያለ ሲሆን በዘር ሊተላለፍ ይችላል፡፡
ለጨረር የመጋለጥ ሁኔታ ፤አንድ ወንድ በደረቱ አካባቢ በጨረር ሕክምና ከተረዳ ምናልባትም በዚያ ሳቢያ የጡት ካንሰር ሊይዘው ይችላል፡፡  
ከላይ የተጠቀሱትና ሌሎችም ለጡት ካንሰር ለመጋለጥ በተለይም ለወንዶች ምክንያት ይሆናሉ ተብለው ተጠቅሰዋል፡፡ የጡት ካንሰር ከምን ደረጃ ላይ ይገኛል የሚለውን ለመለየት የህክምና ባለሙያዎች እንደሚከተለው አስቀምጠዋቸዋል፡፡
ደረጃ 0፤ የጡት ካንሰሩ ምርመራ ሲደረግ በ0/ደረጃ ላይ ያለ ከሆነ የካንሰር ሴሉ ወደሌላ ሰውነት ሊሰራጭ ከማይችልበት ደረጃ ላይ ይገኛል ማለት ነው፡፡
ደረጃ 1፤ በደረጃ አንድ ላይ የሚገኝ የካንሰር ሴል በጊዜው የህክምና እርዳታ ካልተደረገለት ወደሌላ ሰውነት ሊሰራጭ እንደሚችል አመላካች ነው፡፡
ደረጃ 2፤ የካንሰር ሴሉ በደረጃ ሁለት ላይ ከተገኝ ትናንሽ የካንሰር ሴሎች በቡድን ወደአጎራባች የሰውነት ክፍሎች የተሰራጨ መሆኑን እና በእርግጥ ወደ ቲዩመር/ወይንም ወደዋናው የካንሰር መገለጫ እንዳላደጉ ወይም ደግሞ ከ2/ሴንቲ ሜትር በላይ ያላደገ ቲዩመር መኖሩን ይናገራል፡፡ በዚሁ በደረጃ ሁለት ቀጣዩ ነገር ወደሌሎች የሰውነት ክፍሎች ሊሰራጭ የሚችል የካንሰር ሴል መኖሩን እና እርዝመቱም ከ2-5 ሴንቲሜትር የሚገመት መሆኑን እንዲሁም ወደሌላ የሰውነት ክፍል መተላለፍ አለመተላለፉን በሚመለከት እርግጠኛውን ለመናገር የማያ ስችል ነው፡፡ አንዳንድ ጊዜ እስከ 2/ሴንቲሜትር የሚደርስ ቲዩመር ወደሌላ የሰውነት ክፍል ተላልፎ ሊገኝ ይችላል፡፡ የካንሰሩ ደረጃ በዚህ መልክ እድገቱን እየጨመረ የመስፋፋት አቅሙ ንም እያጠናከረ እስከ 5/አምስተኛ ደረጃ ድረስ ይቀጥላል፡፡ በደረጃ አራት ላይ የሚታየው  የጡት ካንሰሩ ወደሌላ የሰውነት ክፍል ተሰራጭቶ  ለከፍተኛ ሕመም የሚዳርግበትና በሕክምናም ለማዳን አስቸጋሪ የሚሆንበት ደረጃ ሲሆን ደረጃ 5/አምስት ደግሞ የመጨረሻው ክፍል ነው፡፡
        ምንጭ፡- Breast Cancer.com
የጡት ካንሰር መከላከያ ዋና መፍትሄ የሚባለው የህክምና ክትትል ማድረግ ነው ያሉን ዶ/ር መብራቱ ጀምበር የጽንስና ማህጸን ሕክምና ባለሙያ ናቸው፡፡ ዶ/ር ከዚህም በተጨማሪ የገለጹት እራስን መመርመር እንዴት ይቻላል የሚለውን ነው፡፡ ካንሰሩ መኖር አለመኖሩን ለመለየት ራስን በራስ መመርመር  ጠቃሚ ነው፡፡ ሰውነትን ሙሉ በሙሉ ወይም ግማሽ አካልን በሚያሳይ መስታወት ፊት ለፊት ቆሞ ሁለት እጅን ከሁዋላ ማጅራት ላይ በማስቀመጥ ጡት ወደፊት እንዲፈጥ በማድረግ የጡት ቆዳ ለስለስ ያለ ወይንም የተጨማደደ ነገር እንዳለበትና እንደሌለበት ማየት አንዱ ዘዴ ነው፡፡ ጡት በተፈጥሮው አፍንጫው አካባቢ ጠቆር ያለ ነው። ከተለመደው ውጪ የተለየ ጥቁረት ወይም የነጣ የገረጣ ለማሳከክም የሚጋብዝ ነገር ካለ ቶሎ  ማየት ያስፈልጋል። እንደገናም ጡትን በሃሳብ አራት ቦታ በመክፈል አራቱን ቦታዎች በጣት በመዳሰስ እጢ ወይም እብጠት.. የጓጐለ ነገር መኖር አለመኖሩን ማረጋገጥ ይገባል፡፡ ሌላው እራስን የመመርመሪያ ዘዴ ደግሞ ገላን በሚታጠቡበት ጊዜ ገላን ሳሙና ከቀቡ በሁዋላ ሲዳሰስ በበለጠ ተፈጥሮአዊ ያልሆኑ ነገሮችን ለማግኘት ያስችላል ፡፡ የጡትን አካባቢ ብቻ ፈትሾ ማቆም ደግሞ በቂ አይደለም ፡፡ወደብብትም ገብቶ በመዳሰስ እብጠት መኖር አለመኖሩን ማረጋገጥ ያስፈልጋል፡፡