Administrator

Administrator

 የፌደራል ትራንስፖርት ባለስልጣን የአሽከርካሪዎች ማሰልጠኛ ተቋማት ገምጋሚ በጥራት በማሰልጠን በስራ አፈፃፀማቸው የመረጣቸውን ማሰልጠኛ ተቋማት ሸለመ ከአዲስ አበባ ዮዮ የአሽከርካሪዎች ማሰልጠኛ ተቋም ተሸላሚ ሆኗል፡፡
በጥራት አሰልጥኖ ብቁ ሾፌሮችን እያወጣ ነው ለተባለውና ከአዲስ አበባ ተቋማት 1ኛ የወጣው ዮዮ የአሽከርካሪዎች ማሰልጠኛ ተቋም የዋንጫ እና የሰርተፍኬት ሽልማት አግኝቷል፡፡
ጥቅምት 17 ቀን 2009 በተደረገው በዚህ የሽልማት ስነ ስርአት ላይ በክልል ያሉ ሌሎች የማሰልጠኛ ተቋማትም መሸለማቸው ታውቋል፡፡
2003 ዓ.ም የተመሰረተው ዮዮ የአሽከርካሪዎች ማሰልጠኛ ተቋም በሁሉም የመንጃ ፍቃድ የስልጠና ዘርፎች ላይ ስልጠና በመስጠት ላይ ይገኛል፡፡

በመቄዶንያ የአረጋውያንና የአዕምሮ ህሙማን ማዕከል ላሉ ከ1 ሺህ በላይ አረጋውያንና የአዕምሮ ህሙማን በነገው ዕለት በአለምገነት ቆርቆሮ ፋብሪካ ባለቤቶች የምሳ ግብዣ ያደርጋል፡፡
በምሳ ግብዣው ላይ ሁሉም ህብረተሰብ እንዲታደም የተጋበዘ ሲሆን በዝግጅቱ ላይ የሃይማኖት አባቶች፣ ታዋቂ ግለሰቦችና ጥሪ የተደረገላቸው በሺህ የሚቆጠሩ እንግዶች ይገኛሉ ተብሏል፡፡
ማዕከሉ በአሁን ወቅት ከመንግስት ባገኘው 30ሺህ ካሬ ሜትር ቦታ ላይ ለአረጋውያን ምቹ የሆነ መኖሪያ ተገንብቶ አገልግሎት እየሰጠ ይገኛል፡፡
ከአረጋውያንና አዕምሮ ህሙማኑ ጋር በማዕከሉ በመገኘት ልደት፣ ሰርግ፣ ኒካ፣ ቀለበት፣ መልስ፣ ሰዲቃ፣ የሙት መታሰቢያ፣ ምርቃት እና ሌሎች ዝግጅቶች ማድረግና አረጋውያኑን መመገብ እንደሚቻልም ማዕከሉ አስታውቋል፡፡ 

መነሻ
ባለፈው ሳምንት በወጣው “ቁምነገር” መጽሄት ላይ የጸሀፌ ተውኔት አያልነህ ሙላቱ ቃለመጠይቅ ታትሞ ነበር፡፡ በሁለት ክፍል ያሳተማቸው ግጥሞች ላይ የተሰነዘሩ ትችቶች አሉ ወይ? ብሎ ጋዜጠኛው ላቀረበለት ጥያቄ እንዲህ ሲል መለሰ፡
‹‹ፊት ለፊት መጥቶ የነገረኝ ሰው የለም፡፡ አንድ ግን ዶ/ር በድሉ የሚባል ሰው በጋዜጣ ላይ ትችት ጽፎ ነበር፡፡ በኋላ ራሱ ይቅርታ ጠይቋል፡፡ እንዴት ነው የተቸኸው ሲባል፣ በየ 100 ገጹ አንዱን ግጥም አንብቤ ነው የምተቸው አለ፡፡ ይሄ ምን አይነት ንቀት ነው፡፡ በፍጹም እንዲህ አይደረግም፡፡ ትልቅ ስህተት ነው፡፡ ደራሲው የጻፈበትን ርእዮተ አለምስ አይተኸዋል ወይ ሲባል፣ ‹ይሄ ምን ርእዮተ አለም አለው› አለ፡፡ ሰዎች ናቸው ይህን የሚነግሩኝ፡፡ የኔ ግጥም እኮ የተጻፈው በሶሻሊስት ርእዮተ አለም ላይ ተመስርቶ ነው፡፡ ‹ይሄን ርእዮተ አለም ሳታውቅ እንዴት ጻፍክ?› አሉት፡፡ ከዚያ፣ ‹ይቅርታ፣ እኔ ይህንን አላወቅኩም ነበር አለ፡፡ በድሉ ጥሩ ገጣሚ ነው፡፡ ስራዎቹንም አንብቤለታለሁ፡፡ ቢሆንም ግን የኔን ግጥም ለመተቸት ብቃቱ ያለው አይመስለኝም። . . . እንዲያውም በእሱ ላይ የሆነ ልጅ መልስ ጽፎ ነበር፡፡ ግን “አዲስ አድማስ” ጋዜጣ ወስዶ ሲሰጣቸው አይታተምም ብለው ከለከሉት፡፡ በጣም ነው ያዘንኩት፡፡ ቢታተም ኖሮ መከራከሪያ ነጥብ ይሆን ነበር፡፡ ለውይይት በር ይከፍታል፡፡ ግን እምቢ አሉት፡፡›› (ቁምነገር፣ ቅጽ 15፣ ቁጥር 270፡፡)
በዚህ አንቀጽ ከሰፈረው የጋሽ አያልነህ ንግግር ያለው እውነት አንድ ብቻ ነው፤ የእኔ ስም፡፡ ግራ ተጋባሁ፡፡ የእጅ ስልኬን አነሳሁና ጋሽ አያልነህ ዘንድ ደወልኩ፤ ስልኩ ተይዟል፡፡ ቆይቼ ደወልኩ፤ ይጠራል፡፡ አላነሳውም፡፡ ከአንድ ሰአት በሁዋላ ደወልኩ፡፡ ስልኩ ተዘግቷል፡፡ ሲከፈት እንዲነገረኝ አንድን ጨቁኜ ዘጋሁት፡፡ ይህ የሆነው ቅዳሜ ነው፡፡ እሁድ አልፎ ሰኞ መጣ፤ ስልኩ አልተከፈተም፡፡ ሰኞ እለት የ”ቁም ነገር” መጽሄት አዘጋጅ ዘንድ ደወልኩ፡፡ የሰፈረው መረጃ ሀሰት መሆኑን ስነግረው፣ ‹‹እንዴት ሊሆን ይቻላል? ጋሼ አያልነህ አይዋሽም፤ ትልቅ ሰው ነው፡፡›› አለኝ፡፡ አያይዞም፣ እንደሚያናግረውና ማስተባበያ ካለው እንደሚያትመው ገልጸልኝ፡፡ እራሴን ተጠራጠርኩት፡፡ የጋሽ አያልነህ ግጥሞች የታተሙ ሰሞን ሚዩዚክ ሜይዴይ በሚያዘጋጀው ሂሳዊ ውይይት ላይ፣ ለውይይት መነሻ የሚሆን ሀሳብ፣ እራሱ ጋሽ አያልነህ ባለበት እንዳቀረብኩ ትዝ ይለኛል፡፡ በጋዜጣ ግን በፍጹም አልጻፍኩም፡፡ ምን አልባት ለውይይት ያቀረብኩትን አትመውት ይሆን? በወቅቱ የሚዩዚክ ሜይዴይ አስተባባሪ የነበረው በፍቃዱ አባይ ስለነበር በእጅ ስልኩ ላይ ደወልኩ። ሁኔታውን በዝርዝር ገለጥኩለት፡፡ ለዚያ ውይይት ያቀረብኩት መነሻ ሀሳብ በየትኛውም ጋዜጣ እንዳልታተመ ገለጠልኝ፡፡ አያይዤም፣ ‹‹ለመሆኑ በውይይቱ ላይ ይቅርታ ጠይቄው ነበር እንዴ?›› ስል ጠየኩት፡፡ ‹‹በጭራሽ! እንዲያውም መጨረሻ  ላይ እኮ እራሱ ጋሽ አያልነህ፣ ‹ስሜታዊ ሆኜ በድሉን ያስቀየምኩት ይመስለኛል፤ ይቅርታ ልጠይቅ ብሎ› ይቅርታ የጠየቀው እሱ ነው፤ ካስፈለገ እኮ ሙሉ ውይይቱ በምስል መቅጃ ተቀድቷል፡፡›› አለኝ። “አዲስ አድማስ” ጋዜጣ አዘጋጅ ዘንድ ደወልኩ፤ ‹‹በእኔ ስም ጋሽ አያልነህ ግጥሞች ላይ የታተመ ሂስ አለ እንዴ?›› ጠየቅኩ፡፡ ‹‹ኧረ በጭራሽ›› መለሰልኝ፡፡ ‹‹እሺ የሆነ ልጅ መልስ አምጥቶ ለምን አናትምም አላችሁ?›› ደግሜ ጠየቅኩ፡፡ ‹‹እንዴ! መጀመሪያ አንተ ካልጻፍክ መልስ እንዴት ይመጣል?›› በጥያቄ መለሰልኝ፡፡ ‹‹እሺ መልስም አይሁን፣ ስለ ጋሽ አያልነህ ግጥሞች፣ የተጻፈ፤ የእኔን ስም የሚጠቅስ ጽሁፍ መጥቶላችሁ ነበር?›› ደግሜ ጠየቅኩ፡፡ ‹‹ኧረ በፍጹም!››፡፡
ማክሰኞ ጠዋት የስልኬ የመልእክት ማሳበቂያ ድምጽ ጮኸ፡፡ ከፍቼ ሳነበው፣ ‹ጋሽ አያልነህ ስልኩን ከፍቷል፤ አሁን ብትደውል ታገኘዋለህ ይላል›፡፡ ደወልኩለት፡፡ ተነሳ፡፡
‹‹ሀሎ ጋሽ አያልነህ››
‹‹ማን ልበል?››
‹‹በድሉ ነኝ፡፡››
‹‹አያልነህ መኪና እየነዳ ነው፤ ‹ከደቂቃዎች በኋላ እደውልልሀለሁ› እያለህ ነው፡፡››
‹‹ጥሩ፡፡ በቁምነገር መጽሄት ላይ እኔን ጠቅሶ የተናገረውን እንዳነበብኩትና ስለዚያ ጉዳይ ላነጋግረው እንደምፈልግ ንገርልኝ፡፡››
‹‹እነግረዋለሁ፡፡ ይደውልልሀል፡፡››
አንድ ሰአት. . . ሁለት ሰአት አለፈ፤ አልተደወለም። እኔ ደወልኩ፡፡ መጥራት እንደጀመረ ጥሪው ተጨናገፈ፡፡ ደግሜ ደወልኩ፤ አሁንም ተጨናገፈ፡፡ ከዚያ በኋላ ያለው ምርጫ ሁለት ነው፡፡ አንድ፣ ንቆ መተው፡፡ ሁለት፣ እሾህን በሾህ እንዲሉ፣ የሚዲያውን ሁከት በሚዲያ ማጥራት፡፡ እኔ ሁለተኛውን መረጥኩ፡፡ ንቆ መተው፣ ይሉኝታ . . . የሚባሉት እሴቶች፣ በመቻቻልና በመከባበር አብሮ ለመኖር ትልቅ ዋጋ ቢኖራቸውም፣ ያለ ቦታቸው ሲገቡና ደፋር ሆን ብሎ ሲጠቀምባቸው የሀሰትን፣ የበደልንና የእስስታዊነትን ጡንጫ ያደነድናሉ፡፡ በተለይ እንደ ጋሽ አያልነህ አይነት በእድሜ አንጋፋና ታዋቂ ሰው በርካታ ወጣቶች ላይ ሊያሳድር የሚችለው ተጽእኖ ቀላል ስላልሆነ፣ እንዲህ አይነቱን ‹ጅብ ወለደ› ንቆ መተው፣ በተለይ እንደኔ ግማሽ እድሜውን መምህር ሆኖ ለኖረ፣ ሀላፊነትን ያለመወጣትም ጭምር ነው፡፡  
በጋሽ አያልነህ ንግግር ላይ መልስ ለመስጠት ከወሰንኩ በኋላ፣ ጽሁፌ ምን አይነት መሆን፣ ምን ምን ጉዳዮች መያዝ አለበት? ብዬ እራሴን ጠየቅኩ። በ‹‹እንዲህ ብለሀል!  . . . እንዲህ አላልኩም!››  ብቻ የታጀለ ፍሬ ከርስኪ እንዲሆን አልፈለግኩም፡፡ ጋሽ አያልነህ ‹‹ . . እንዲህ አለ አሉ›› ብሎ የጠቃቀሳቸውን ሀሳቦች፣ ከ‹‹አለ አሉ›› የሀሜት ግርግም አውጥቼ፣ ከእውቀትና እውነት መስክ ላግጣቸው ወደድኩ፡፡
ለምን ይዋሻል!?
ጋሽ አያልነህ፣ በጸሀፊነት የማውቀህ የመጀመሪያ ዲግሪ የቋንቋና ስነጽሁፍ ተማሪ ከነበርኩበት፣ ከ1980ዎቹ መጀመሪያ አንስቶ ነው፡፡ በእሳት ሲነድ፣ ትግላችን፣ ሻጥር በየፈርጁ፣ የመንታ እናት. . . ወዘተ. በመሳሰሉት አብዮታዊ ተውኔቶቹ አውቅሀለሁ፡፡  
ጋሽ አያልነህ ትዋሻለህ፡፡ ‹‹. . ዶ/ር በድሉ የሚባል ሰው በጋዜጣ ላይ ትችት ጽፎ ነበር፡፡›› አልክ፤ እኔ በየትኛውም ጋዜጣ ትችት አልጻፍኩም፤ ጋዜጣውን አምጣና ሞግተኝ፡፡ በአንድ ውይይት ላይ ለውይይት የሚሆን የመነሻ ሀሳብ በቃል አቅርቤያለሁ፡፡  ‹‹በኋላ ራሱ ይቅርታ ጠይቋል፡፡›› አልክ፤ እኔ አንተን ይቅርታ አልጠየቅኩም፡፡ ይቅርታ ያልጠየቅሁ ይቅርታን ስለምጸየፍ ወይም የተሸናፊነትና የአሽናፊነት መግለጫ አድርጌው አይደለም፡፡ ባጠፋ እንኳን አንተን ታላቄን፣ ታናሼንም ይቅርታ እጠይቃለሁ፡፡ አንተ ግን ይቅርታ መጠየቅን የተሸናፊነት መገለጫ አድርገህ ትመለከተዋለህ፡፡ ይህን ያስባለኝ፣ አዳራሽ ሙሉ ሰው በተሰበሰበበት፣ ውሉ ዝግጅቱ በምስል መቅጃ በተቀዳበት ዝግጅት መጨረሻ ይቅርታ የጠየከኝ አንተ ሆነህ ሳለ ገለበጥከው፡፡ ምነው እኔ አጥፍቼ በሆነና ይቅርታ በጠየቅኩህ (በነገራችን ላይ ዘንግተኸው ከሆነ ሚዩዚክ ሜይዴይ የተቀረጸው ፊልም አለ)፡፡ ጋሼ በጣም ያዘንኩት በአንተ ላይ ብቻ ሳይሆን፣ በሰው ልጅ ላይ ያለኝን እምነት የፈተነብኝ፣ ‹‹ፊት ለፊት መጥቶ የነገረኝ ሰው የለም፡፡. . . . . ሰዎች ናቸው ይህን የሚነግሩኝ፡፡›› ያልከውን ሳነብ ነው፡፡ ምነው ጋሼ! አዳራሽ ሙሉ ሰው ፊት፣ መድረክ ላይ ተቀምጠን፣ ወጣት በፍቃዱ አባይ ውይይታችንን እየመራው፣ የግጥሞችህን ጉድፎች ያልኩትን ፊት ለፊት አልነገርኩህም?  
ጋሼ አንድ ጸሀፊ ለቤተሰቡ፣ ለወገኑ፣ ሲልቅም ለሰው ልጆች ክብር ሊኖረው ይገባል፡፡ ለዚህ ሁሉ መሰረቱ ግን ራስን ማክበር ነው፡፡ የጸሀፊው የራስ ክብር ደግሞ መሰረቱ እውነትን በየትኛውም ሁኔታ ውስጥ (ህይወቱን የሚያስከፍለው ቢሆን እንኳን) ለመመስከር ያለው ቆራጥነት ነው፡፡ ራስህን ለእውነትና ፍትህ ስታስገዛ፣ ለማህበረሰብህ እውነትና ፍትህን ትመግበዋለህ፡፡ ከዚህ አንጻር ለራስህ ክብር የለህም ብልህ ቅር ይልህ ይሆን? ለራስህ ክብር ቢኖርህ እንደምን እንዲህ ያለ የሀሰት ቅሌት ውስጥ አያልነህን ትጨምረዋለህ? ‹‹እንዴት ነው የተቸኸው ሲባል፣ በየ 100 ገጹ አንዱን ግጥም አንብቤ ነው የምተቸው አለ፡፡ ይሄ ምን አይነት ንቀት ነው፡፡ በፍጹም እንዲህ አይደረግም፡፡ ትልቅ ስህተት ነው። ደራሲው የጻፈበትን ርእዮተ አለምስ አይተኸዋል ወይ ሲባል፣ ‹ይሄ ምን ርእዮተ አለም አለው› አለ፡፡ የኔ ግጥም እኮ የተጻፈው በሶሻሊስት ርእዮተ አለም ላይ ተመስርቶ ነው፡፡ ‹ይሄን ርእዮተ አለም ሳታውቅ እንዴት ጻፍክ?› አሉት፡፡ ከዚያ፣ ‹ይቅርታ፣ እኔ ይህንን አላወቅኩም ነበር አለ።››  በየ100 ገጹ አንድ ግጥም ብወስድማ፣ 1156 ገጽ ካለው አንዱ መጽሀፍህ ውስጥ 11 ግጥሞች ብቻ ነበር የሚሆነው፡፡ እኔ ግን ሌላው ቀርቶ ጋሼ፣ በዘጠኝ ቀን የእስር ቤት ቆይታህ (ከግንቦት 28 ቀን 1996 እስከ ሰኔ 7 ቀን 1969) የጻፍካቸውን ወደ 22 የሚጠጉ ግጥሞች ገምግሜ፣ ‹‹አንድ ጓድ ለሌላው ጓድ የጻፋቸው ደብዳቤዎች ይመስላሉ፤አንተ ራስህ በመግቢያህ ውስጥ ስለ ግጥም ያስቀመጥካቸውን ባህርያት አያሟሉም.›› ብዬህ ነበር፡፡
ሌላው የተሟገትንበት ነጥብ፣‹ ‹በድሉ ሶሻሊዝምን አያውቅም፤ የተማረው አሜሪካ ስለሆነ ሶሻሊዝምን ይጠላል፡፡›› ስትል፣ የተማርኩት አሜሪካ ሳይሆን ኖርዌይ መሆኑን አስተካክዬህ፣ ስለ ሶሻሊስት ሪያሊዝም ስነጥበባዊ ፍልስፍና ተነጋግረን ነበር፡፡ አሁንም ደግሜ ልንገርህ ጋሼ፣ በየዘመኑ የተጻፉ ስነጽሁፎችን ለመገምገም በየዘመኑ መኖር አያሻም፤ እንዲያ ቢሆን ለሀምሌትና ኦቴሎ የሼክስፒር ዘመነኛ ሀያሲ ከየት አባታችን እናመጣ ነበር! ስለ የዘመኑ ስነጥበባዊ ፍልስፍና እና ስለየ ስራዎቹ ባህርያት ማወቅ፣ በንባብ የመተንተንን አቅም ማዳበር ለአንድ ሀያሲ በቂው ነው፡፡ በነገራችን ላይ ጋሼ፣ ሶሻሊዝምን እንዳንተ በቅርብ ባይሆንም፣ በመኖርም አውቀዋለሁ፡፡ ገና በ11 አመቴ፣ በጠዋት የኪራይ ወተት ሳመጣ፣ ከደጃችን ላይ ክብ ሰርቶ የከበበውን ሰው፣ ግራ ቀኝ ሰርስሬ ስገባ፣ ቀይ ሽብር የጣለውን የጎረቤታችንን የእንሰሳት ሀኪሙን የዶ/ር መክብብ ተሰማን ሬሳ ስመለከት፣ከእጄ ካመለጠው የወተት ሽጉጥ (የቢራ ጠርሙስ ሽጉጥ ይባል ነበር) የፈሰሰው ወተት አፈሩ ላይ ከረጋው ደም ጋር ሲደባለቅ የፈጠረው ህብረ ቀለም ዛሬም ደምቆ ይታየኛል፡፡ ‹‹ሁሉም ለአብዮታዊት እናት ሀገር ዘብ ይቁም!›› ብላችሁ ባወጃችሁት የብሄራዊ ውትድርና አገልግሎት፣ ገና 18 አመት ልደፍን መንፈቅ ሲቀረኝ ከትምህርት ቤት ታፍሼ፣ የሁለት አመት ከመንፈቅ ግዳጄን ተወጥቻለሁ፡፡ እና ጋሼ እንዳንተ ባልንቦጫረቅበትም፣ እንደ አንድ የዘመነ ደርግ ወጣት ሶሻሊዝምን በመኖርም በመጠኑ አውቀዋለሁ፡፡
‹‹እንዲያውም በእሱ ላይ የሆነ ልጅ መልስ ጽፎ ነበር፡፡ ግን “አዲስ አድማስ” ጋዜጣ ወስዶ ሲሰጣቸው አይታተምም ብለው ከለከሉት፡፡ በጣም ነው ያዘንኩት፡፡ ቢታተም ኖሮ መከራከሪያ ነጥብ ይሆን ነበር፡፡ ለውይይት በር ይከፍታል። ግን እምቢ አሉት፡፡›› ላልከውም ተደራቢ ውሸትና (ካፈርኩ አይመልሰኝ) መሆኑን የጋዜጣው አዘጋጆች አረጋግጠውልኛል፤ እና ጋሼ ግን ለምን? እንዳንተ ያለ አንጋፋ፣ የኢትዮጵያን ደራስያን ማህበርን በምክትል ሊቀመንበርነት የሚመራ፣ ብዙ ወጣቶች በአርአያነት ቀና ብለው የሚመለከቱት ሰው ለምን ይዋሻል? አንድ የሰውን ልጅ እታደጋለሁ የሚል ደራሲ፤ እንደምን ከዚህ አይነቱ ውሸት ጋር አደባባይ መቆም ይቻለዋል?
የደራሲው እውነት ወዴት አለች!?
የደራሲ እውነት የግሉ እውነት ብቻ አይደለም፤ እንዲያውም ማህበራዊና ሰብአዊ እውነቱ ነው ጸሀፊን በማህበሰቡ ውስጥ የመሪነት ሚና የሚያጎናጽፈው፡፡ በዚህ ረገድ አኔና አንተ በዘመናችን እንደ አቤ ጉበኛና በአሉ ግርማ ያሉ ስለ ሰው ልጅ እውነት መስዋእት የሆኑ ደራስያን እናውቃለንና ታድለናል። ለሰው ልጅ እውነት ለመቆም የሚውተረተር ነፍስ ካለንም ድጋፍ ልናደርገው እንችላለን፡፡ ጋሼ መቼም አደባባይ ቆመን እንድንነጋገር መርጠሀልና እስቲ ስለዚህ አይነቱ የደራሲ እውነት እንነጋገር፡፡ ከአንተ ዘንድ ይህች የደራሲው ማህበራዊና ሰብአው እውነት አለችን? እኔ አታውቃትም ብዬ እማኝ ጠቅሼ እሞግትሀለሁ። እማኝ የምጠቅሰው አንተኑ ነው፤ ተግባርና አንደበትክን፡፡
ባለፈው ሳምንት በዚያው በ”ቁምነገር” መጽሄት ላይ እንዲህ ብለሀል፤ ‹‹ዛሬ የኢትዮጵያ ኪነጥበብ ህዝብ እየመራ አይደለም፡፡ በመሰረቱ ኪነጥበብ ህዝብን መምራት አለበት፡፡›› ልክ ብለሀል ጋሼ፤ እኔም በዚህ ነጥብ እስማማለሁ፡፡ ስለዚህ ሁላችንም እንደ አቅማችን የምንኖርበት ማህበረሰብ መንገዱን ያስተውልበት ዘንድ ጭላንጭል ለመፈንጠቅ እንሞክራለን፡፡ የሚገርመው ግን ይህ አባባልህ ከሰበካነት አልፎ የደራሲ ነፍስህ ግብር አለመሆኑ ነው፡፡ ‹‹እኔ በደርግ ውስጥ የነበርኩ ሰው ነኝ። በእዚያ ውስጥ እያለሁ ምን እጽፍ ነበር? በአንድ በኩል ለእንጀራ የሚሆን ስራ ትሰራለህ፡፡›› ትላለህ፣ እዚያው ቃለመጠይቅ ውስጥ፡፡ ‹‹ለእንጀራ›› ማለት ምን ማለት ነው ጋሼ? በደርግ ዘመን ወጣቶች ላመኑበት፣ ለሀገርና ማህበረሰብ ይበጃል ላሉት እውነት መስዋእት ሲሆኑ፣ ደራስያን ባመኑበት እውነት ፍቅር ተነድፈው ሲጠፉ፣ አንተ ለእለት እንጀራ ትጽፍ ነበር! እስቲ ልጠይቅህ፤ ትግላችንን፣ የመንታ እናትን፣ ሻጥር በየፈርጁን፣ እሳት ሲነድን . . . .  ጽፈህ የበላኸው እንጀራ ምን ምን ይላል? ይህን የምጠይቅህ ለምን አብዮቱን በብእርህ አፋፋምክ፣ ደገፍክ ብዬ አይደለም፡፡ ብዙዎች በደርግ ዘመን ስለ አብዮቱ ጽፈዋል፡፡ ‹ሶሻሊዝም የሀገራችንን ህዝቦች ለዲሞክራሲና ለብልጽግና ያበቃል፤ በህዝቦች መካከል እኩልነትን ያሰፍናል› ብለው ከልብ አምነው እንጂ፣ለእለት ጉርስ ብለው ግን አይደለም። ባለቅኔውንና ጸሀፌ ተውኔቱን ደበበ ሰይፉን ታውቀዋለህ፡፡ ለሶሻሊዝም የነበረው እምነት መቼም ከሀይማኖት የላቀ ነበር፡፡ ‹መስከረም›፣ ‹በስሙ ሰየማት›፣ ‹ትዝታ ከበሮ›ን የመሳሰሉት ግጥሞቹ፣ደበበ ሶሻሊዝምን ምን ያህል ከልቡ ያምንበት እንደነበር ከማሳየታቸውም በላይ፣ እውነቱና ምናቡ  ተቃቅፈው ያዘመሩትን ቅኔ ምጥቀት ይመሰክራሉ። ደበበ ከደርግ መውደቅና ከሶሻሊዝም ቀብር በኋላ፣ የኖረውን ኑሮና መጨረሻውን የምታውቅ ይመስለኛል፡፡ በአሉንም ከእኔ በተሻለ ታውቀዋለህ። ጋሼ እንዲህ ያለችው እውነት አንተ ዘንድ የለችም፡፡ ትላንት እውነቴና እምነቴ ነው ብለህ፣ ‹እሳት ሲነድን› ያንቀለቀልክለትን አብዮት፣ ዛሬ እንጀራ ገዶኝ ነው ማለት፣ በዚህኛው ዘመንም ማኛ ለማነጎት ምጣድ ከማስማት የዘለለ ፋይዳ የለውም፡፡


የፌስ ቡክ ተከታዮቹ ከ1 ሚሊዮን በላይ ሆነዋል

ቃና ቴሌቪዠን የተመልካቾቹን የመዝናኛ አማራጭ ለማጎልበት ሁለት አዳዲስ ዝግጅቶችን (አንድ ወጥ እና አንድ በአማርኛ የተመለሰ) ማቅረብ መጀመሩን ገለጸ፡፡
በአሁኑ ጊዜ ጣቢያው በየሳምንቱ የ30 ሰዓት አዳዲስና ያልታዩ ዝግጅቶችን ለተመልካቹ እንደሚያቀርብ በላከው መግለጫ አስታውቋል፡፡
ሰሞኑን 5ኛ ክፍሉ የተሰራጨው የ #ምንድን ዝግጅት፣ የተለያዩ ወቅታዊ ማሕበረሰብ ተኮር ርዕሶችን እያነሳ ከተለያዩ ምልከታዎች አንጻር የሚያወያይ ሲሆን በዚህም የተመልካቾችን ተሳትፎና ጤናማ ውይይቶች ያበረታታል ተብሏል። አዲስ የተጀመረው “ልጅቷ” የተባለው የኮሎምቢያ ድራማ፤ በእውነተኛ ክስተቶች ላይ የተመረኮዘ ሲሆን የጦርነትን አስከፊ ገጽታ ያሳያል፡፡ ታሪኩ አንዲት ሴት በሽምቅ ተዋጊዎች ተመልምላ የጦርነትን አስከፊ ገፅታ በአፍላ እድሜዋ እንድትኖረው ስትገደድና ከብዙ ዓመት በኋላ አምልጣ አዲስ ኑሮ ለመጀመር ስትሞክር፣ ከሕብረተሰብ ጋር ለመቀላቀል፣ ነፃነትዋን ለመልመድና ቤተሰብዋን ለመጋፈጥ የሚደርስባትን ውጣ ውረድ ያስቃኛል፡፡ ድራማው ከፍተኛ አድናቆትን ያገኘ ሲሆን በቅርቡ ኔትፍሊክስ በተባለው ታዋቂ የፊልም አቅራቢና አከፋፋይ ተገዝቶ፣ በብዙ አገሮች እየታየ ይገኛል ብሏል - ቃና በመግለጫው፡፡
በተመልካቾች ዘንድ ተወዳጅነትን ያተረፈውን ጥቁር ፍቅር የተሰኘ ድራማ የሚተካ ቅጣት የተባለ ወደ አማርኛ የተመለሰ የቱርክ ድራማ በቅርቡ ማቅረብ እንደሚጀምር ጠቁሞ ቅጣት በይዘቱ ልክ እንደ ጥቁር ፍቅር በተለያዩ አገሮች ዝና እና ሽልማት ተቀዳጅቷል ተብሏል፡፡
ጣቢያው የተመልካቾቹን ዕይታ ለማበልፀግና ፍላጎታቸውን ለመገንዘብ፣ በየጊዜው የተለያዩ ጥናቶችና ዳሰሳዎች እንደሚያካሂድ ጠቁሞ ግኝቶችንም በሚያቀርባቸው ዝግጅቶች ላይ እንዲንፀባረቁ ይደረጋል ብሏል፡፡
በስርጭት ላይ በቆየበት የስድስት ወር ጊዜያት ውስጥ ጥሩ አቀባበል ማግኘቱን የጠቀሰው ቃና.፤ የፌስ ቡክ ተከታዮቹ ከ1 ሚሊዮን በላይ መድረሳቸውን አስታውቋል፡፡ በቅርቡ በቤል ካሽ የተካሄደ በ 5000 ሰዎች ላይ የተደረገ አገር አቀፍ የስልክ መጠይቅ፤ ከሶስት ተጠያቂዎች ውስጥ አንዱ የቃና ቴሌቪዥን ዝግጅቶችን ከሰኞ እስከ አርብ በየቀኑ እንደሚያዩ አመልክቷል፡፡
“ቃና ቴሌቪዥን በሕብረተሰቡ ዘንድ ያለው አቀባበል አበረታችና ከጠበቅነው በላይ ነው። ወደፊትም  የመዝናኛ አማራጭ የሆኑ አዝናኝና አሳታፊ ዝግጅቶችን ለማቅረብ የተመልካቾቻችንን ፍላጎት ማጥናት እንቀጥላለን” ብለዋል፤ የቃና ቴሌቪዥን የኮሙኒኬሽን እና ማርኬቲንግ ዳይሬክተር፡፡  
ቃና ቴሌቪዥንና የዝግጅት አጋሩ ቢ ሚዲያ በቅርቡ ይፋ የሚሆኑ ተጨማሪ ወጥ ስራዎችን እያዘጋጁ እንደሚገኙም ለማወቅ ተችሏል፡፡  

“የፖሊሲ ለውጥ ከሌለ የግለሰቦች መቀያየር ለውጥ አያመጣም”

• ተቃዋሚዎችና ፖለቲከኞች በሹም ሽሩ ደስተኞች አይደሉም
• የህዝቡን ጥያቄዎች መለስ ብሎ ማየት ያስፈልጋል ተባለ
ኢህአዴግ ሥልጣን ከያዘ በኋላ በኦሮሚያና በአማራ ክልሎች በተቀሰቀሰው ታይቶ የማይታወቅ ህዝባዊ አመፅና ተቃውሞ በአጠቃላይ ወደ አንድ ሺ የሚጠጉ ዜጎች ህይወታቸውን ያጡ ሲሆን በብዙ ሺዎች የሚገመቱ በእስር ላይ እንደሚገኙ ዓለም አቀፍ የሰብአዊ መብት ተሟጋች ተቋማትና የተቃዋሚ ፓርቲዎች ሪፖርት ይጠቁማል፡፡ የሟቾች ቁጥር ተጋንኗል የሚለው መንግስት በበኩሉ፤የጸጥታ ሃይሎችን ጨምሮ ከ500 በላይ ሰዎች መሞታቸውን አልካደም፡፡  በተቃውሞው በርካታ የመንግስትና የግል ባለሃብቶች ንብረትም እንደተቃጠለና እንደወደመ መዘገቡ ይታወሳል፡፡
ይሄን የፖለቲካ ቀውስ ተከትሎ ነው በኢህአዴግ የሚመራው መንግስት፤የከፍተኛ ባለስልጣናትን ሹም ሽር የሚያካትት “ጥልቅ ተሃድሶ” በማድረግ የህዝቡን ጥያቄዎች እንደሚመልስ በ2008 መጠናቀቂያ ላይ ቃል የገባው፡፡ በዚህ መሃል በኦሮሞ ባህላዊ የምስጋና ቀን “እሬቻ” በዓል ላይ በተከሰተው አስደንጋጭ የበርካታ ዜጎች ህልፈት ሳቢያ ህዝባዊ ቁጣ ተቀሰቀሰ፡፡ በቀጣዮቹ ቀናትም በተለይ የውጭ ባለሃብቶችን ክፉኛ ያስደነገጠ ውድመትና ዘረፋ በፋብሪካዎቻቸው፣በእርሻቸው፣በአጠቃላይ በንብረቶቻቸው ላይ ተፈጸመ፡፡ ይሄን ተከትሎም የዛሬ ሦስት ሳምንት መንግስት አገሪቱን ለማረጋጋትና የህዝቦችን ሰላም ለማስጠበቅ በሚል ለ6 ወር የሚቆይ የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ ማወጁን አስታወቀ፡፡
ባለፈው ማክሰኞ ጠ/ሚኒስትር ኃይለማርያም ደሳለኝ በግንቦት 200ገ ምርጫ ማግስት ራሳቸው ያቋቋሙትን የሚኒስትሮች ካቢኔት በመበተን፣ከወትሮው በተለየ መንገድ በምሁራን የተዋቀረ አዲስ ካቢኔ የመሰረቱ ሲሆን 9 ሚኒስትሮች ብቻ ባሉበት ሲቀሩ 16 አዳዲስ ሚኒስትሮችን ሾመዋል፡፡ ከእነዚህ ውስጥ 5 የሚሆኑት የፓርቲ አባል አይደሉም ተብሏል፡፡ ሹመቱ የተከናወነው በዋናነት የትምህርት ዝግጅትና ብቃትን መሰረት አድርጎ መሆኑን ለተወካዮች ም/ቤት የገለጹት ጠ/ሚኒስትሩ፤አዳዲሶቹ ሚኒስትሮች የህዝብን ጥያቄ ለመመለስ አቅሙና ብቃቱ ያላቸው እንደሆኑ ተናግረዋል፡፡
 የተቃዋሚ ፓርቲ አመራሮችና ፖለቲከኞች ግን በአዲሱ ካቢኔ ደስተኛ አይደሉም፡፡ በምሁራን በተዋቀረው አዲስ ካቢኔም እምብዛም የተደመሙ አይመስሉም፡፡ ጠንከር ያለ ሂስ የሰነዘሩም አልጠፉም። ሁሉም በአንድ ድምጽ የሚስማሙበት ግን የፖሊሲ ለውጥ አስፈላጊነት ላይ ነው፡፡ የፖሊሲ ለውጥ ሳይደረግ ግለሰቦች መለዋወጥ ብቻውን ውጤት አያመጣም ባይ ናቸው፡፡ የህዝቡም ጥያቄዎች በዚህ መንገድ መልስ ያገኛሉ ብለው እንደማያምኑ አበክረው ይናገራሉ፡፡ አንጋፋዎቹን የተቃዋሚ ፓርቲ አመራሮችና ፖለቲከኞች በአዲሱ ሹም ሽር ዙሪያ ጋዜጠኛ አለማየሁ አንበሴ አነጋግሯቸዋል፡፡      
                                                           ****

“ዋናው መሰረታዊ ጉዳይ የፖሊሲ ለውጥ ነው”
ዶ/ር መረራ ጉዲና
(የፖለቲካ ሳይንስ ምሁርና የተቃዋሚ መሪ

*የሰሞኑን የሚኒስትሮች ሹመት እንዴት አገኙት? እንደጠበቁት ነው ወይስ ----?
“ፍየል ወዲህ ቅዝምዝም ወዲያ” እንደሚባለው ነው የሆነው፡፡ ህዝብ እየጠየቀ ያለው መሰረታዊ ለውጥ ነው፡፡ ኢህአዴግ ደግሞ ቀባብቶ ለማለፍ እየሞከረ ነው፡፡ ከኋላ የነበሩትን ወደፊት በማምጣት “ይኸው እየተሻሻልኩ ነው፤እየተለወጥኩ ነው፤ እየታደስኩ ነው” እያለ ነው፡፡ ህዝብ ግን የጠየቀው፡- ነፃ ምርጫ ቦርድ፣ ነፃ ፍርድ ቤት፣ ነፃ ሚዲያ፣ ነፃ የሲቪክ ተቋማትና ሌሎች ብዙ ጉዳዮችን ነው። ራስን በራስ ማስተዳደር ሌላው የህዝብ ጥያቄ ነው፡፡ ኢህአዴግ ግን “እኔ ራሴ እየተለወጥኩ ነው እመኑኝ፤ ጥያቄያችሁን እየመለስኩላችሁ ነው” አይነት ነገር ነው እያለ ያለው፡፡
*ሹመቶቹ የትምህርት ዝግጅትንና ብቃትን መሰረት አድርገው የተሰጡ ናቸው ተብሏል፡፡ ከዚህ አንጻር ከቀድሞው የተሻለ ውጤት መጠበቅ አይቻልም?
ኢህአዴግ አሁን ከገባበት አጣብቂኝ ውስጥ ግለሰቦችን በመለዋወጥ የሚወጣ አይመስለኝም። ለህዝቡም ጥያቄ አጥጋቢ መልስ አይመስለኝም። ለምሳሌ ብዙ የእውቀት ሰርተፍኬት ያላቸው ሰዎች ገብተዋል ነው የተባለው፡፡ በኢህአዴግ ውስጥ ያለው ችግር ግን የእውቀት ብቻ አይደለም፤ መሰረታዊ የፖሊሲ ችግር አለ፡፡ የአሰራር ችግር አለ፡፡ ያንን የሚለውጥ ነገር መፈጠር ነው ያለበት። ግለሰቦች ብቻ መለዋወጡ፣ “ጉልቻ ቢቀያየር ወጥ አያጣፍጥም” ነው የሚሆነው፡፡ እነዚህ ተሾሙ የተባሉ ምሁራኖችም ቢሆኑ በኢህአዴግ አካባቢ የነበሩ ናቸው፡፡ አዳዲሶች አይደሉም፡፡ በተለያየ ደረጃ ኢህአዴግን ሲያገለግሉ የቆዩ ናቸው፡፡ ምን ውጤት እንደሚያመጡ ለወደፊት የምናየው ይሆናል፡፡
*በምክትል ጠ/ሚኒስትር ማዕረግ የሚሉትን ጨምሮ የጠ/ሚኒስትሩ አማካሪነት ሹመቶች እንዲቀሩ ተደርገዋል፡፡ በዚህ ላይ የእርስዎ አስተያየት ምንድን ነው?
እነዚህ የስልጣን እርከኖች ከህገ መንግስቱ ውጪ የነበሩ ናቸው፡፡ አንድ ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር እንጂ በርካታ ምክትል ጠ/ሚኒስትሮችና አማካሪዎች ይኖራሉ የሚል አንቀፅ ህገ መንግስቱ ላይ የለም። ስልጣንን ለማደላደል የተደረገ እንጂ ህጋዊ አልነበረም፡፡ ዞሮ ዞሮ ያመጡትም የወሰዱትም እነሱ ናቸው፡፡ ስለዚህ ይህን በማስቀረታቸው የሚመጣ ብዙ ለውጥ የለም፡፡ እንዳልኩት ዋናው መሰረታዊ ጉዳይ የፖሊሲ ለውጥ ነው፡፡ ፖሊሲው ከተለወጠ በኋላ የተሻለ ስራ መስራት ያስችላል፡፡ ላለፉት 25 ዓመታት ተሞክሮ አሁን ያለውን ቀውስ ያስከተለውን ፖሊሲ ሳይለውጡ፣ ባለስልጣናትን ወደ ፊትና ወደ ኋላ በማድረግ ምንም ውጤት ሊመጣ አይችልም፡፡ እንደ አንድ የፖለቲካ ሳይንስ መምህር፣ በዚህ በኩል ምንም የሚታየኝ ነገር የለም፡፡
አዲሱ ካቢኔ በዚህ መልኩ በምሁራን ይዋቀራል ብለው ጠብቀው ነበር?
ምን መጠበቅ ያስፈልጋል! ተሃድሶ እናደርጋለን እያሉን አልነበር እንዴ፡፡ እኔ ግን ይሄን አልነበረም የጠበቅሁት፡፡ የፖሊሲ ለውጥ ነበር የምጠብቀው። “እኔ ማስተዳደር አቅቶኛል፤ከሌሎች ኃይሎች ጋር መግባባት ፈጥሬ፣ከምሁራን ጭምር ተቀናጅቼ ለውጥ አመጣለሁ” ቢል ነበር መልካም የሚሆነው። የሠለጠነ ሃገር ቢሆን ኖሮ፣ ይሄ መንግስት የኢትዮጵያን ህዝብ ይቅርታ ጠይቆ ከስልጣን መውረድ ነበረበት፡፡ ብዙ ቃል የገባቸውን ነገሮች መፈፀም ስላቃተው፣ ”ስልጣን ወይም ሞት” ማለቱን ትቶ፣ ቢሆን ከስልጣን መውረድ ካልሆነ ደግሞ ከኢትዮጵያ ምሁራን ጋር ተቀናጅቶ፣የዲሞክራሲ ስርአት ግንባታ ለመጀመር ቁርጠኝነቱን ማሳየት ነበረበት፡፡
የፖሊሲ ለውጥ የሚሉትን ሊያብራሩልኝ ይችላሉ?
የፖሊሲ ለውጥ ሲባል ለምሳሌ ነፃና ፍትሃዊ ምርጫ አንዱ ነው፡፡ የዴሞክራሲ ተቋማት ነፃነት፣ ለምሳሌ የሚዲያ ነጻነት፣ የፍርድ ቤት ነጻነት፣ የፓርላማ ነፃነት ---- ሌላው ነው፡፡ ይሄ ሲሆን ነፃና ፍትሃዊ ምርጫ ተግባራዊ ሊደረግ ይችላል፡፡ የስልጣን ክፍፍል ማድረግም አንድ የፖሊሲ ለውጥ ጉዳይ ነው፡፡ ሌላው ህዝቡ በመረጣቸው የአካባቢ አስተዳደሮች እንዲመራ ማድረግ ነው፡፡
መሬትን በተመለከተ “መድረክ” መሬት ይሸጥ የሚል አቋም የለውም፤ ነገር ግን ለምሳሌ መንግስት መሬቱን ሲሸጥ ከሚያገኘው ገንዘብ ላይ ለገበሬው በተገቢው መልኩ ማካፈል አለበት፡፡ እነሡ አሁን 50 ሺህ ብር ካሳ ከፍለው ወዲያው ያንን ቦታ 50 ሚሊዮን ብር ይሸጡታል፡፡ ነገር ግን ከ50 ሚሊዮኑ ለገበሬው 10 ሚሊዮኑን መስጠት ይቻል ነበር፡፡ በቦታው ላይ 50 መኖሪያ ቤቶች ከተሰሩ ደግሞ 10ሩን ለባለ መሬቱ ሰጥቶ፣ እያከራየ ህይወቱን እንዲለውጥ ማድረግ ይቻላል፡፡ በዚህም ገበሬው የተሻለ ህይወት ሊመራ ይችላል፡፡ ዋናው ነገር ኢኮኖሚውንም የዲሞክራሲ ጨዋታ ማድረግ ያስፈልጋል፡፡  
የምርጫ ስርአቱ ይሻሻላል ተብሏል፡፡ ስርአቱ መሻሻሉ ምን የሚያመጣው ለውጥ ይኖራል?
በፊት ከነበረው ይሻላል እንጂ መሠረታዊ ለውጥ አያመጣም፡፡ ባለፉት 16 እና 17 አመታት የአንድ ፓርቲ የበላይነት እንዲቀንስ ስንጠይቅ ነበር። አሁን ኦሮሚያ ውስጥ ነፃና ፍትሃዊ ምርጫ ቢደረግ ኢህአዴግ በዝረራ ይሸነፋል፡፡ የሆኖ ሆኖ የምርጫ ሥርዓቱ መሻሻሉ አይጠላም፡፡ እኛም ስንጠይቀው የነበረ ነው፡፡ ግን መሠረታዊ መፍትሄ አይደለም። አሁን ህዝብ እየጠየቀ ያለው ከዚያም የላቀ ነው፡፡ ራስን በራስ የማስተዳደር ጉዳይ አንዱ ጥያቄ ነው፡፡

==============================

“በምሁራን የተዋቀረ የመጀመሪያው ካቢኔ ነው”
አቶ ልደቱ አያሌው (ፖለቲከኛ)

የካቢኔ ሹም ሽረቱን እንዴት ገመገሙት? ለውጥ የሚያመጣ ይመስልዎታል?
እኔ እንደጠበቅሁት አላገኘሁትም፡፡ ትንሽ ወጣ ብሎ ለህብረተሰቡ ጥሩ አስተዋፅኦ ሊያደርጉ የሚችሉ ግለሰቦችን ሊያካትት ይችላል የሚል ግምት ነበረኝ፡፡ ግን ያ ሆኖ አላገኘሁትም፡፡ አንደኛ የተቋቋመውን ካቢኔ “የምሁራን ካቢኔ” ልንለው እንችላለን፡፡ አሁንም በዋናነት የታየው አንደኛ የፓርቲ ታማኝነት ነው፤ ሁለተኛ የትምህርት ደረጃ ነው፡፡ እኔ ሁለቱም ብቻቸውን ውጤታማ የሆነ የህዝብ አስተዳደር ለማምጣት ያስችላሉ ብዬ አላምንም፡፡ የስራ ልምዳቸው ሲዘረዘር፣ ከአንድ ወይም ሁለት ሰው በስተቀር አብዛኞቹ በኢህአዴግ መዋቅር ውስጥ ባለፉት 15 ዓመታት የነበሩ ናቸው። አዲስ አመለካከት፤ አዲስ እይታ ያለው ሰው አልተቀላቀለም፡፡ ሁለተኛ፤ አንድ ሰው ሚኒስትር እንዲሆን የሚፈለገው ቴክኒካል የሆነ ምርምር እንዲሰራ አይደለም፡፡ ሚኒስትር ለመሆን በአንድ ነገር ላይ የረቀቀ እውቀት አይፈልግም። ሚኒስትርነት የበለጠ የፖለቲካ አመራር ብቃትን ይጠይቃል። ብዙ ጊዜ በኛ ሀገር ብቻ ሳይሆን በዓለም ሁኔታ የምናውቀው፣ የአካዳሚ ሰዎች የአመራርነት ሚናቸው በጣም ዝቅተኛ መሆኑን ነው፡፡ በምሁርነት የቆዩ ሰዎች ወደ አመራርነት ሲመጡ፣ እውቀታቸውን በአግባቡ እንዳይጠቀሙ ነው የሚሆኑት፡፡  
ምናልባት አሁን በሚሉት ጉዳይ ላይ አለማቀፍ ተሞክሮ ይኖር ይሆን?
የጠቅላይ ሚኒስትሩ ካቢኔ በዚህ ደረጃ ከተዋቀረ በኋላ የተለያዩ የመረጃ አማራጮችን በመጠቀም አለማቀፍ ተሞክሮዎችን ለማየት ሞክሬያለሁ። የደረስኩበት መረጃ፣ አዲሱ ካቢኔ በዓለም ላይ በምሁራን የተዋቀረ የመጀመሪያው ካቢኔ መሆኑን ነው፡፡ ይህ የካቢኔ አደረጃጀት በዓለም ላይ የመጀመሪያዎቹ ሊያደርገን ይችላል፡፡ ሌሎች ሃገሮች ያልተደረገ ነው፡፡ ሚኒስትርነት ፖለቲካን የማስተዳደር፣ ውሳኔ የመስጠት ብቃትን የሚጠይቅ እንጂ ሙያን የሚጠይቅ አይደለም፡፡ ግለሰቡ በአንድ ጉዳይ ላይ ምርምርና ጥናት ማድረጉ አይደለም መታየት ያለበት፡፡
ዋናው የሚኒስትር መስሪያ ቤቱን የተለያዩ ዲፓርትመንቶች አስተባብሮ አቀናጅቶ መምራት መቻሉ ነው፡፡ ዶክተሮችና ምሁራንን መመደብ ብቻውን ለውጥ ያመጣል ብዬ አላምንም። አንድ ሁለት ሰዎችን ነው ወጣ ያለ የስራ ልምድ ያየሁባቸው፡፡ ሌሎቹ በአጠቃላይ በኢህአዴግ ውስጥ የኖሩ ናቸው፡፡ አዲስ አቀራረብና አሰራር ይዘው ለመጡ የሚችሉ አይመስለኝም፡፡ ከዚህ አንፃር ካቢኔው የሚፈለገውን ውጤት ያመጣል ብዬ አላምንም፡፡ ምናልባት አሁን ከተፈጠረው ቀውስ አንፃር ብሄረሰባዊ ተዋፅኦውን ጎላ አድርጎ በመሾም ሁኔታዎችን ለማርገብ የተፈለገ ይመስላል፡፡ ይሄ ግን አጉል ጨዋታ ነው የሚሆነው፡፡
ህብረተሰቡም እየጠየቀ ያለው ይሄን አይደለም። አቶ እገሌ ወርዶ፣ ዶ/ር እገሌ ይሾምልኝ አይደለም ያለው፡፡ የፖለቲካ ለውጥ ነው እየጠየቀ ያለው። ከዚህ አንፃር በቂ የሆነ ጥናትና ግምገማ ተካሂዶ፣ ለወቅቱ ችግር አስተዋፅኦ ሊያደርግ የሚችል ካቢኔ፣ በቅጡ ታስቦበት የተቋቋመ አልመሰለኝም። ቢቻል ከኢህአዴግ ወጣ ብሎ የሌላ ፖለቲካ ፓርቲ አባላትም ቢሆኑ፣ ህብረተሰቡን ለማገልገል ፍቃደኝነቱ እስካላቸው ድረስ ማካተት ቢቻል ጥሩ ነበር፡፡ ያ ባይሆን እንኳ ነፃና ገለልተኛ የሆኑ ሰዎችን ከንግዱ ማህበረሰብ፣ በሲቪል ተቋማት ከሚገኙ ምሁራን  ማካተት ይቻል ነበር፡፡ እንዲህ ዓይነት ሰዎችን በአዲሱ ካቢኔ ውስጥ አላየናቸውም። ከሲቪል ሰርቪስ ኮሌጅ ጀምሮ በወረዳ መዋቅር ውስጥ የነበሩና የሚያውቋቸውን ሰዎች ነው ለሹመት  ያቀረቡት፡፡
አንዳንድ ፖለቲከኞች “የሚያስፈልገው የፖሊሲ ለውጥ ነው” ሲሉ ይከራከራሉ፡፡ የእርስዎ አቋም ምንድን ነው?
 አንዱ የስርአቱ ችግር የወቅቱን የህዝብ ተቃውሞና የብሶት እንቅስቃሴ ከአፈፃፀም ችግር ጋር አያይዞ ማየቱ ነው፡፡ ተቃውሞው በመልካም አስተዳደርና በኢኮኖሚ አፈፃፀም ጉድለት ሳቢያ ብቻ የመጣ አድርጎ ነው የሚመለከተው፡፡ የተቃውሞውን መሰረታዊ ምንጭ በደንብ ከመረመርነው ግን ችግሩ ፖለቲካዊም ነው፡፡ ስለዚህ ፖለቲካዊ መፍትሄ ካልመጣ በስተቀር ይሄን ችግር መፍታት አይቻልም፡፡ ለጊዜው በአስቸኳይ ጊዜ አዋጁ ችግሩን መቆጣጠር ይቻላል፡፡ ነገ ከነገ ወዲያ ግን በዘላቂነት ችግሩን መቆጣጠር ያዳግታል፡፡ ስለዚህ መለስ ብሎ የችግሩን ምንጭ በጥልቀት መመርመር ያስፈልጋል። በዚህ ከተማመንን የችግሩን ምንጭ የማወቅ ጉዳይ ለኢህአዴግ ብቻ መተው የለበትም፡፡ የፖለቲካ ፓርቲዎች፣ ህዝቡ መወያየት አለባቸው፡፡
ኢህአዴግ ብቻውን ለምንድን ነው የሚወስነው? የችግሩ ምንጭ ላይ መተማመን ካልተቻለ፣ በመፍትሄው ላይ መተማመን ላይ መድረስ አይቻልም፡፡ ኢህአዴግ የችግሩ ምንጭ ይህ ነው ብሎ በራሱ አይን አይቶ ከወሰነ በኋላ፣ ያንን ለማስፈፀም ነው ጥረት የሚያደርገው፡፡ ይሄ ግን ችግሩን አይፈታውም፡፡
የችግሩ ምንጭ ምንድን ነው? ብለን ከመረመርን፣ መሰረታዊ የሆኑ የፖለቲካ ችግሮች መኖራቸውን እንገነዘባለን፡፡ ያንን መፍታት የሚቻለው የአፈፃፀም አቅምን በማጎልበት ብቻ አይደለም፤ የፖሊሲ ለውጥ በማምጣት ነው፡፡ ከህገ መንግስቱ ጀምሮ የፌደራል አደረጃጀቱ የየራሳቸው ችግሮች አሉባቸው፤ እነሱ መሻሻል ይገባቸዋል፡፡ በሌላ በኩል በህገ መንግስቱም ሆነ በሌላ ህጎችም የተቀመጡ ጥሩ ጥሩ ህጎች መሬት ላይ መውረድ አለባቸው፡፡ ከወረቀት አልፈው ተግባር ላይ ሊውሉ ይገባል፡፡ የችግሮቹ መነሻ እነዚህ ነገሮች ናቸው፤ መፍትሄውም የሚገኘው ከእነዚህ ነው፡፡
ገዥው ፓርቲ ግን በጣም ቅንጭብጫቢ የሆኑ ከሙስና፣ ከመልካም አስተዳደር ጉዳዮች ጋር የተያያዙ ችግሮችን በመፍታት ብቻ ለውጥ አመጣለሁ እያለ ነው፡፡ ይሄ ግን ብቻውን መፍትሄ አይሆንም፡፡ ባለፉት 25 ዓመታት በተለያዩ የመዋቅር ማሻሻያዎች ለመፍታት ተሞክሮ የከሸፈ ነው፡፡ የችግሩ ምንጭ ያለው የፖለቲካ ሙስና ውስጥ ነው፤ የፖለቲካ ሙስና ሳይፈታ የኢኮኖሚ ሙስና ሊፈታ አይችልም፡፡ ኢህአዴግ የችግሩን መሰረታዊ ምንጭ አላወቀም ወይም ለማወቅ አልፈለገም፡፡
ተቃዋሚዎች በተደጋጋሚ፤ ”ኢህአዴግ ምሁራንን አያሳትፍም፤ ሙያን ለሙያተኛ አይለቅም” የሚል ትችት ሲሰነዝሩ እንደነበር ይታወቃል፡፡ ይሄ ከእርስዎ አስተያየት ጋር እንዴት ይታረቃል?
ሚኒስትርነት የፖለቲካ ሹመት ነው፡፡ የሚፈለገው ውጤትም በሚኒስቴር መስሪያ ቤቱ ያሉ የተለያዩ ዲፓርትመንቶችን አቀናጅቶ መምራት ነው። ከስራው ጋር ቀጥተኛ ሙያዊ ግንኙነት ያላቸው ሰዎች ምክትል ሆነው ሊሰሩ ወይም የዲፓርትመንት ኃላፊ ሆነው ሊመደቡ ይችላሉ፡፡ ትችቱ ከዚህ አንፃር ነው መታየት ያለበት፡፡ ለምሳሌ የማህፀን ሃኪም ናቸው ብሎ ማብራሪያ መስጠት ከሚኒስትርነት ጋር ምንም ግንኙነት የለውም፡፡
የጤና ጥበቃ ሚኒስትር ለመሆን በአንድ ውስን ሙያ ላይ ኤክስፐርት መሆን አይፈልግም፡፡ የሚኒስትርነት ቦታው ሙያዊ አይደለም፤ ፖለቲካዊ ነው፡፡ የሚፈለገው የአመራር ብቃት ነው፡፡ ጠቅላይ ሚኒስትር የግድ የፖለቲካ ሳይንስ ምሁር ወይም የህግ ምሁር መሆን አይጠበቅበትም፤ ዋናው የአመራር ክህሎቱ ነው፡፡ ሙያተኞች ምክትል ሆነው ሊሰሩ ይችላሉ፡፡     


===============================

“ዋናው ጥያቄ ዲሞክራሲያዊ ስርአት የመመስረት ነው”
ዶ/ር ያዕቆብ ኃ/ማርያም (ዓለማቀፍ የህግ ባለሙያ)

    ጠቅላይ ሚ/ሩ ያዋቀሩትን አዲስ ካቢኔ እንዴት አዩት?
እኔ ብዙም ለውጥ የሚያመጣ አይመስለኝም። ምክንያቱም የሰው ችሎታ ማነስ አይደለም የችግሩ ምንጭ፡፡ ዋናው ጥያቄ የፖሊሲ ጥያቄ ነው እንጂ በግለሰቦች ያለመርካት አይደለም። ዋናው መሰረቱ ፖሊሲ ነው፡፡ የፖሊሲ ለውጥ እስካልመጣ ድረስ በአዕምሮ ምጡቅ ነው የተባለ ሰው እንኳ ስልጣን ላይ ቢቀመጥ ለውጥ ላያመጣ ይችላል። ህዝቡ በተደጋጋሚ ሲጠይቃቸው ከነበሩት ጥያቄዎች መረዳት የሚቻለው፣ የፖሊሲ ጉዳዮችን የሚያስፈትሹ መሆናቸውን ነው።  ዋናው ሲጠየቅ የነበረው ዲሞክራሲን የማስፈን ጉዳይ ነው፡፡ ዲሞክራሲያዊ ስርአት ከተተገበረ ሌሎቹ ጥያቄዎች በዚያ አግባብ ምላሽ ያገኛሉ፡፡ የምርጫ ስርአቱ ስለሚሻሻል በህዝብ የተመረጠው ግለሰብ በሙስና ቢጨማለቅ፣ ህዝቡ በድምፁ መልሶ እንደሚያባርረው ያውቃል፡፡ ስለዚህ ዋናው ጥያቄ ዲሞክራሲያዊ ስርአት የመመስረት ነው፡፡ የሚዲያዎች ነፃነት፣ የፍርድ ቤቶች ነፃነት፣ የሲቪክ ተቋማት ነፃነት ጥያቄ ነው፡፡ የግለሰቦች ለውጥ አይደለም ጥያቄው፡፡ የግለሰቦች መቀያየር ያን ያህል ለውጥ የሚያመጣ አይመስለኝም፡፡
የፖሊሲ ለውጥ ሲሉ ለምሳሌ--ይጥቀሱልኝ?
ነፃ ምርጫ፣ የፓርቲዎች ነፃነት፣ የጋዜጦችና የሚዲያ ነፃነት፣ የፍ/ቤቶች ነፃነት ---- በተለይ  ለህግና ለህሊናቸው እንዲገዙ ማድረግ የመሳሰሉ መሰረታዊ የፖሊሲ ማሻሻያዎች መደረግ አለባቸው። እነዚህ አሁን በሀገራችን እንደሌሉ ይታወቃል። እነዚህ መሰረታዊ ለውጦች እስካልተደረጉ ድረስ የሰዎች መለዋወጥ ትርጉም የለውም፡፡ ይህን ለውጥ ለማምጣት ደግሞ ኢህአዴግ ዝግጁ አይመስለኝም፡፡
ምሁራን ወደ ሚኒስትርነት መምጣታቸው አስተዳደራዊ መዋቅሮችን በእውቀት ለመግራት አስተዋፅኦ አይኖራቸውም?
እርግጥ ነው ምሁራን የተሻሉ ናቸው፡፡ እውቀቱ ከሌላቸው ሰዎች እውቀቱ ያላቸው የተሻለ እንደሚሰሩ ምንም ጥርጥር የለውም፡፡ ወሳኙ ግን የሚሰሩት ስራ ምንድን ነው የሚለው ነው?   አምባገነንነትን ለማጠናከርም ምሁራን ይሻላሉ፡፡ በዚያው ልክም ዲሞክራሲን ለማምጣት ምሁራን ይመረጣሉ፡፡
የፖለቲካ ምህዳሩ እስካልሰፋ ድረስ ግን የምሁራን መሾም ምንም ዋጋ የለውም፡፡ ምሁርነታቸውንና እውቀታቸውን በአግባቡ አውጥተውም ሊጠቀሙ አይችሉም፡፡

==============================

“ሹም ሽረቱን በበጎ አይን ነው የምመለከተው”

     ዶ/ር ነጋሶ ጊዳዳ (ፖለቲከኛ)

የህዝቡ ጥያቄ ማህበራዊ፣ ፖለቲካዊና ኢኮኖሚያዊ ችግሮች ይፈቱልን የሚል ነው፡፡ ከዚህ አንፃር የተሾሙት ምሁራን የበለጠ በእውቀት ላይ የተመሰረተ አገልግሎት ሊሰጡ ስለሚችሉ ሹመታቸው መልካም ነው፡፡ በሌላ በኩል እነሱ ብቻ ሳይሆኑ ጠቅላላ ስርአቱ የህዝብን ጥያቄ ለመመለስ ብቃቱና ዝግጁነቱ አለው ወይ? የሚለውን በደንብ ፈትሾ፣ የምሁራኑ እውቀት ተጨምሮበት ከተሰራ ጥሩ ነው፡፡ ያ ካልሆነ ግን ምሁራን በተለያዩ ዘርፎች መቀመጣቸው ብቻ የህዝብን ጥያቄ አይመልስም፡፡  
ከዚህ በፊት “የፖለቲካ ስልጣኑ እውቀትና ብቃት ባላቸው ሰዎች ሳይሆን በታማኝ ፖለቲከኞች ብቻ ነው የሚያዘው” የሚለውን ሲያነሱ የነበሩት ራሳቸው ምሁራኑና የፖለቲካ ድርጅቶች ነበሩ። ህዝቡ ይሄን ጥያቄ ያነሳ አይመስለኝም፡፡ ህዝቡ በዋናነት የሚፈልገው ያነሳቸው ጥያቄዎቹ መመለሳቸውን ነው፡፡ ከዚህ አንፃር ኢህአዴግ ምሁራንን መሾሙ ምናልባት “ሰዎች በታማኝነት እንጂ በእውቀት አይመደቡም” ለሚለው መልስ ሊሰጥ ይችላል፡፡ እንደኔ ግን እነዚህ የተሾሙ ሰዎች፤ ዶክተሮች ፕሮፌሰሮችና ምሁራን ቢሆኑም ባይሆኑም ቴክኒካሊ የሚሰጣቸውን ስራ እውቀት ላይ ተመስርተው ይሰራሉ የሚል እምነት አለኝ። ግን እነዚህ ምሁራን የህዝቡን ፖለቲካዊ ችግሮች ይመልሳሉ ወይ ነው ጥያቄው፡፡
ይህን ለመመለስ መንግስትን የሚመራው ድርጅት የሚከተለው ርዕዮተ አለምና ከዚያም በመነሳት የሚያወጣው ፖሊሲ የህዝብን ጥያቄዎች ምን ያህል ይመልሳል የሚለውም መታየት አለበት፡፡ ትልቁ መሰረታዊ ጉዳይ ያለው ፖሊሲው ላይ ነው፡፡
የፓርቲ አባል ያልሆኑ ሰዎችንም የመሾም ሁኔታ እያየሁ ነው፡፡ የአንድ ፓርቲ የበላይነትና ልማታዊ ዲሞክራሲ የሚባለው ርዕዮተ ዓለም፣ የሀገሪቱን ህዝቦች ጥያቄ እየመለሰ ነው ወይ የሚለው ነው ዋናው ጥያቄ። ነባሮቹ እየለቀቁ አዳዲስ ሰዎች ማምጣቱ ጥሩ ነገር ነው፡፡ በአንድ በኩል ይህ ሲደረግ መንግስትና ፓርቲን የመለየት ነገር እየመጣ ነው ማለት ነው፡፡ ግን ሂደቱ በጣም አዝጋሚ ነው። መንግስትና ፓርቲ የተለያዩ መሆናቸውን የበለጠ ማሳየት ያስፈልጋል፡፡ ይሄ ማለት ካድሬ መሆን ብቻውን ለሚኒስትርነት እንደማያበቃ ማሳየት ማለት ነው፡፡ እኔ መልካም አካሄድ ነው ብዬ በበጎ አይን ነው የምመለከተው። በሌላ በኩል የብሄር ተዋፅኦን ከፍ ለማድረግ ተሞክሯል፡፡ ይህ ለህዝቡ ጥያቄ ምን ያህል ምላሽ ሊሰጥ ይችላል የሚለውም በጥልቀት መታየትና መገምገም ይኖርበታል፡፡  


    አስገራሚ ክስተቶች፣ ያልተጠበቁ ሁነቶች፣ አስቂኝ ምልልሶች፣ አስደንጋጭ መረጃዎች፣ ኃይለኛ ፉክክሮች፣ ብዙ ብዙ ትኩረት የሚስቡ ያልተለመዱ ነገሮች የተስተናገዱበት የዘንድሮው የአሜሪካ ፕሬዚዳንታዊ ምርጫ  የፍጻሜው ምዕራፍ ላይ ደርሷል፡፡ የፊታችን ማክሰኞ ይለይለታል፡፡
ማን ይጠበቃል?
በዘንድሮው 45ኛው የአሜሪካ ፕሬዚዳንታዊ ምርጫ፣ እልህ አስጨራሽ ትንቅንቅ ላይ የከረሙት ሁለቱ እጩዎች፣ በምርጫ ቅስቀሳ ዘመቻቸው አንዳቸው ሌላኛቸውን እያብጠለጠሉና እያንኳሰሱ ጎልተው ለመውጣትና የመራጩን ቀልብ ለመግዛት ያልፈነቀሉት ድንጋይ የለም፡፡  በቅድመ ምርጫ ትንበያ ተጠምደው የሰነበቱት ታላላቅ አለማቀፍ መገናኛ ብዙሃንና ተቋማት በምርጫው ማን ያሸንፋል የሚለውን ጥያቄ ለመመለስ የየራሳቸውን ጥናት በመስራት ውጤት ይፋ ሲያደርጉ ሰንበተዋል፡፡ አንዳንዶች የዲሞክራቷን ዕጩ ሄላሪ ክሊንተንን ለአሸናፊነት ሲያጩ፣ ሌሎች አነጋጋሪውን የሪፐብሊን ዕጩ ዶናልድ ትራምፕን ለድል አጭተዋቸዋል፡፡
ዲሞክራቷ ሄላሪ፣ በአንዳንድ የቅድመ ምርጫ ትንበያዎች ለሳምንታት በሰፊ ልዩነት ሲመሩ ቢቆዩም፣ ልዩነቱ ከጊዜ ወደ ጊዜ እየጠበበ መምጣቱና በተለይም ኤፍቢአይ በሄላሪ ላይ የኢሜይል ቅሌት ምርመራ መጀመሩን ማስታወቁን ተከትሎ በአንዳንድ ትንበያዎች ትራምፕ መምራት መጀመራቸው ሲነገር ሰንብቷል፡፡
ኒውዮርክ ታይምስ ከትናንት በስቲያ ባወጣው አገር አቀፍ የቅድመ ምርጫ ትንበያ፣ሄላሪ ቢሊዬነሩን ትራምፕ በሶስት ነጥብ በመምራት ላይ እንደሚገኙ ያስታወቀ ሲሆን፣ ኤቢሲ ኒውስና ዋሽንግተን ፖስት በበኩላቸው፤ ልዩነቱን ወደ ሁለት ዝቅ ያደርጉታል - ለሄላሪ 47፣ ለትራምፕ 45 ነጥብ በመስጠት፡፡
ኦባማም በቅስቀሳ ተጠምደዋል
ሄላሪና ትራምፕ የፖሊሲ አማራጮቻቸውን በማስተዋወቅ፣የተሻለ ያደርገኛል የሚሉትን ነጥብ በማስተጋባት፣ አንዳቸው የአንደኛቸውን ጉድ በመዘክዘክና በማሳጣት የህዝቡን ቀልብ ለመግዛትና የበለጠ ድምጽ አግኝተው ለፕሬዚዳንትነት ለመብቃት በየፊናቸው በምርጫ ቅስቀሳ ቢጠመዱም፣ ኦባማ የትራምፕን ምላስ ለመቋቋም ተስኗቸው አስሬ “ሴት ትንቃለህ” የሚል ነገር የሚደጋግሙትን ሄላሪን ለመደገፍ ባለቀ ሰዓት አደባባይ ወጥተዋል፡፡
የፓርቲ አጋራቸውን ሄላሪን በምርጫ ቅስቀሳ ለመደገፍ ከእነ ሚስታቸው ታጥቀው የተነሱት ፕሬዚዳንት ባራክ ኦባማ፣ አዮዋን ጨምሮ በተለያዩ ስቴቶች በመዘዋወር “ትራምፕ አይበጃችሁም፤ ሄላሪን ምረጡ” በማለት ድምጻቸውን ከፍ አድርገው ሲቀሰቅሱ ሰንብተዋል፡፡ ኦባማ ባለፈው ረቡዕ በኖርዝ ካሮሊና ባደረጉት የምርጫ ቅስቀሳ፣ የዘንድሮውን የአሜሪካ ምርጫ፣ የአሜሪካ ብቻ ሳይሆን የመላው አለም ጉዳይ ጭምር መሆኑን ተናግረዋል፡፡
“ዲሞክራቶች ሆይ!... ይሄ ምርጫ ለአገራችን ብቻ ሳይሆን ለአለም ጭምር ወሳኝ ነው፡፡ ዶናልድ በሚሉት ሰው ሳቢያ፣ የዓለማችን ዕጣ ፈንታሽ አደጋ ላይ ወድቋል፡፡ ይህ ሰው ወደ ስልጣን እንዲመጣ አትፍቀዱለት፡፡ በነቂስ ውጡና ለሄላሪ ድምጻችሁን ስጡ!...” ብለዋል ኦባማ፡፡
መልስ የማያጡት አሽሙረኛው ትራምፕ፤ፍሎሪዳ ውስጥ ሆነው ይሄን ሰሙ፡፡ ሰምተውም እንዲህ አሉ፣ ይላል ቢቢሲ...
“ይሄ ኦባማ የሚሉት ሰው፣ ለሄላሪ  ማሽቃበጡን ትቶ፣ አገሪቱን በመምራቱ ላይ ማተኮር አለበት!...”
ቀድመው የመረጡ
በአሜሪካ ፕሬዚዳንታዊ ምርጫ አሰራር መራጮች ከመደበኛው የድምጽ መስጫ ዕለት በፊት ለሚደግፉት ዕጩ ድምጻቸውን መስጠት ይችላሉ፡፡ በዚህም መሰረት ከ22 ሚሊዮን በላይ አሜሪካውያን፣ ማክሰኞን መጠበቅ ሳያስፈልጋቸው ለመረጡት ዕጩ ድምጻቸውን መስጠታቸውን ዘ ኢንዲፔንደንት ዘግቧል፡፡
ኮሚ ምን ነካቸው?
የምርጫ ቅስቀሳው በተጧጧፈበት፣ አንደኛው የሌላኛውን ዕጩ ድብቅ ገበና በሚያነፈነፉበት፣ የቆየ ወንጀላቸውን ነቅሰው በማውጣት አደባባይ ለማስጣትና ተፎካካሪያቸውን ትዝብት ላይ ለመጣል ደፋ ቀና በሚሉበት፣ ትራምፕ እና ሄላሪ አይጥና ድመት በሆኑበት ወሳኝ ወቅት ላይ፣ያልተጠበቀ ዱብ ዕዳ ተሰማ፡፡
አሜሪካውያን ለሚደግፉት ዕጩ ድምጻቸውን የሚሰጡባት ወሳኝ ዕለት የምትደርስበትን ቀን ሲቆጥሩ ከርመው፣ 11 ቀናት ብቻ ሲቀራቸው፣ ዲሞክራቷን ሄላሪን ክው ያደረገ፣ ሪፐብሊካኑን ትራምፕ በደስታ ያስፈነጠዘ ሰበር ዜና ተሰማ፡፡ የሄላሪን የኢሜይል ቅሌት ክስ መርምሬ፣ አንዳች እንኳን የሚያስከስሳት ወንጀል ባለማግኘቴ ክሱን ወደ መዝገብ ቤት ልኬያለሁ ብሎ የነበረው የኤፍቢአይ ዳይሬክተር ጄምስ ኮሚ፣ ድንገት በቴሌቪዥን መስኮት ብቅ አሉና፣ ሌላ የኢሜይል ቅሌት አግኝተንባታልና ልንመረምራት ነው አሉ፡፡
ሄላሪ ደነገጡ፤ ትራምፕ በደስታ ፈነጠዙ፡፡
“ምን!?...” አሉ ሄላሪ፣ የሰሙትን ባለማመን፡፡
“አላልኳችሁም!?... ይህቺ ወንጀለኛ፣ ገና ወህኒ ትወርዳለች!...” አሉ ትራምፕ፣ ሲሉት የከረሙትን ነገር የሚያረጋግጥ ጮማ ማስረጃ እጃቸው ላይ ሲወድቅ፡፡
“ጄምስ ኮሚ ምን ነካቸው?...” አሉ ብዙዎች በሰሙት ነገር ተገርመው፡፡
ኤፍቢአይ በምርጫ ውጤቱ ላይ ተጽዕኖ የሚፈጥር መሆኑን እያወቀ፣ በወሳኝ ወቅት ይህን አደገኛ ውሳኔ ማሳለፉ ብዙዎች በጥርጣሬ ሲያዩት፣ አንዳንድ የህግ ተንታኞችም የተቋሙን ውሳኔ ህግን ያልተከተለ ብለውታል፡፡ ዳይሬክተሩ ይቅር የማይባል ጥፋት ሰርተዋልና፣ ዛሬ ነገ ሳይሉ ስልጣናቸውን ይልቀቁ ያሉም አልታጡም፡፡ የኤፍቢአይ ውሳኔ የምርጫ ሂደቱን የሚያስተጓጉልና የዲሞክራቷን ዕጩ አሸናፊነት ጥያቄ ውስጥ የሚጥል አደገኛ ነገር ነው ያሉ ተንታኞች የመኖራቸውን ያህል፣ ተጽዕኖው እምብዛም ነው ብለው ያጣጣሉትም አሉ፡፡ ያም ሆነ ይህ ግን፣ የጄምስ ኮሚን መርዶ ተከትሎ፣ የሄላሪና የትራምፕ የቅድመ ምርጫ የአሸናፊነት ትንበያ ልዩነት እየጠበበ ሲመጣ፣ አንዳንዴም ትራምፕ ሲመሩ ታይቷል፡፡
ጠመንጃ ተወዷል!...
የአሜሪካ ምርጫ መቃረቡን ተከትሎ፣በአገሪቱ የጦር መሳሪያ ገበያው መድራቱ ተነግሯል፡፡ ሲኤንኤን እንደዘገበው፣ በአገሪቱ ባለፉት ሶስት ወራት የጦር መሳሪያዎች ሽያጭ ጭማሪ አሳይቷል፡፡ ሽያጩ ባለፈው አመት ተመሳሳይ ጊዜ ከነበረው ጋር ሲነጻጸር ከ30 በመቶ በላይ ጭማሪ አሳይቷል ያለው ዘገባው፣ ባለፉት ሶስት ወራት ብቻ የ161. 4 ሚሊዮን ዶላር የጦር መሳሪያ መሸጡን ገልጧል፡፡
የዚህ ሰበብ ደግሞ፣ ዲሞክራቷ ሄላሪ ናት ይላል ዘገባው፡፡
በአገረ አሜሪካ ምርጫው መቃረቡን ተከትሎ የጦር መሳሪያ ግብይቱ የተጧጧፈው፣ አገሬው ዲሞክራቷ ሄላሪ ታሸንፍ ይሆናል ብሎ በመስጋቱ ነው ተብሏል። እሷ ካሸነፈች ደግሞ የጦር መሳሪያ ቁጥጥሩን የበለጠ ታጠብቀዋለች፣ ስለዚህ አበክሮ መሸመት  ያወጣል በሚል ነው ምድረ አሜሪካዊ ጠመንጃ ገበያ የወረደው ብሏል - ዘገባው፡፡
እሷም እንደ ኮንጎ?...
ከሳምንታት በፊት...
የዲሞክራሲ ባህል ያበበባት፣ ህገ መንግስታዊ ስርዓት የሰፈነባት፣ በስርዓት የሚገዛ ፖለቲካ ስር የሰደደባት ልዕለ ሃያል አሜሪካ፣ ለሺህ ዘመናት ወደ ኋላ ተንሸራትታ እነ ኮንጎ የተዘፈቁበት አዘቅት ውስጥ ልትነከር ማቆብቆብ ጀመረች እንዴ? የሚያሰኝ አጉል ነገር ሆነ፡፡ በዲሞክራሲያዊ ምርጫ ስልጣን የሚያዝባት፣ የምርጫ  ስርዓቷ ነጻና ፍትሃዊነቱ ጥያቄ ውስጥ የማይገባባትን አሜሪካን ለመምራት ታጥቀው የተነሱት፣ የእነ አብርሃም ሊንከንን ወንበር ለመቆናጠጥ የቋመጡት አነጋጋሪው ትራምፕ፣ በመጨረሻው ዙር የምርጫ ክርክራቸው ሌላ አነጋጋሪ ብቻ ሳይሆን፣ የአሜሪካን ዲሞክራሲ ቁልቁል የሚጎትት ነገር ተናገሩ፡፡
“እሷ ካሸነፈች፣ ውጤቱን በጸጋ ለመቀበል ያዳግተኛል!...” አሉ ትራምፕ፡፡
ትራምፕ እንዲህ ማለታቸውን ተከትሎ፣ አሜሪካም እንደእነ ኮንጎ በምርጫ ሳቢያ ብጥብጥ ውስጥ ትገባ ይሆናል የሚል ስጋት መፈጠሩን የአሜሪካ ድምጽ ሬዲዮ ዘግቧል፡፡
ዩኤስኤ ቱዴይ እና ሱፎልክ ዩኒቨርሲቲ በቅርቡ በጋራ በሰሩት ጥናት፣ ድምጻቸውን ይሰጣሉ ተብለው ከሚጠበቁት አሜሪካውያን 51 በመቶው፣ ከምርጫው ጋር በተያያዘ በአገሪቱ ብጥብጥ ይነሳል የሚል ስጋት እንዳላቸው ጠቁመዋል፡፡ ጆ ዋልሽ የተባሉት የቀድሞ የአሜሪካ ኮንግረስ አባል ስጋት ግን ከዚህም ያልፋል ይላል - ዘገባው፡፡
“ማክሰኞ ድምጼን ለትራምፕ እሰጣለሁ፡፡ ረቡዕ ማለዳ ትራምፕ ተሸንፏል የሚል ነገር ከሰማሁ ግን፣ጠመንጃዬን መወልወሌ አይቀርም!... እናንተስ?...” ብለዋል ዋልሽ ሰሞኑን በትዊተር ገጻቸው ባሰፈሩት ስጋት አቀጣጣይ ወጋቸው፡፡
የአሜሪካ ዕድሜ ጠገብ የዲሞክራሲ ሥርዓትና ባህል፣እንደ ዘንድሮም ተፈትኖ አያውቅም፡፡ ከዓይን ያውጣው!!

*በምክትል ጠ/ሚኒስትር ማዕረግ የክላስተር ሹመት ቀርቷል
*9 ሚኒስትሮች ባሉበት ይቀጥላሉ
የህዝብ ጥያቄን ለመመለስ በኢህአዴግ የሚመራው መንግስት ጥልቅ ተሃድሶ አደርጋለሁ ባለው መሰረት
ጠ/ሚኒስትር ኃይለማርያም ደሳለኝ በዛሬው ዕለት የአዳዲስ ሚኒስትሮችን ሹመት ለህዝብ ተወካዮች
ም/ቤት ይፋ አድርገዋልCC ም/ጠቅላይ ሚኒስትሩን ጨምሮ 9 ሚኒስትሮች ባሉበት ሃላፊነት የቀጠሉ ሲሆን
የጠ/ሚኒስትር አማካሪነት ማዕረግ መቅረቱ ታውቋልCC ጠ/ሚኒስትር ኃይለማርያም ደሳለኝ በተሾሙ ማግስት
የተጀመረው በምክትል ጠ/ሚኒስትር ማዕረግ የክላስተር አስተባባሪነት ሹመትም አስፈላጊ አይደለም ተብሎ
ስለታመነበት ቀርቷል ተብሏልCC አዳዲሶቹ ሚኒስትሮች የተሾሙት የትምህርት ዝግጅታቸውንና የመምራት
ብቃታቸውን መሰረት አድርጎ በመሆኑ የተሰጣቸውን ሃላፊነት በተሻለ መልኩ ይወጣሉ ብለው እንደሚያምኑ
ጠ/ሚኒስትሩ ተናግረዋልCC በግንቦት 2007 ምርጫ ሁሉም መቀመጫዎቹ በኢህአዴግ አባላት የተሞላው
የህዝብ ተወካዮች ም/ቤት፣በጠ/ሚኒስትሩ የቀረቡትን አዳዲስ ተሹዋሚዎች በሙሉ ድምጽ አጽድቆታልCC
የአዳዲሶቹ ሚኒስትሮች ስም ዝርዝርC-
1. የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር - ዶ/ ር ወርቅነህ ገበየሁ
2. የፐብሊክ ሠርቪስና የሰው ሃብት ሚኒስትር - አቶ ታገሠ ጫፎ
3. የንግድ ሚኒስትር - ዶ/ ር በቀለ ሙላቱ
4. የገንዘብና ኢኮኖሚ ትብብር ሚኒስትር - ዶ/ ር አብርሃም ተከስተ
5. የእንስሳትና አሳ ሃብት ሚኒስትር - ፕ/ ር ፍቃዱ በየነ
6. የእርሻና ተፈጥሮ ሃብት ሚኒስትር - ዶ/ ር እያሱ አብርሃም
7. የሣይንስና ቴክኖሎጂ ሚኒስትር - ዶ/ ር ኢ/ ር ጊታሁን መኩሪያ
8. የትራንስፖርት ሚኒስትር - አቶ አህመድ ሺዴ
9. የከተማ ልማትና ቤቶች ሚኒስትር - ዶ/ ር አምባቸው መኮንን
10- የኮንስትራክሽን ሚኒስትር - ኢ/ ር አይሻ መሃመድ
11- የውሃ መስኖ ኤሌክትሪክ ሚኒስትር - ዶ/ ር ኢ/ ር ስለሺ በቀለ
12- የማዕድን ነዳጅና ተፈጥሮ ሚኒስትር - አቶ ሞቱማ መቃሣ
13- የአካባቢ ደንና የአየር ንብረት ሚኒስትር - ዶ/ ር ገመዶ ዳሌ
14- የትምህርት ሚኒስትር - ዶ/ ር ሽፈራው ተ/ ማርያም
15- የጤና ጥበቃ ሚኒስትር - ፕ/ ር ይፍሩ ብርሃኔ
16- የመንግስት ልማት ድርጅት ሚኒስትር - ዶ/ ር ግርማ አመንቴ
17- የባህልና ቱሪዝም ሚኒስትር - ዶ/ ር ሂሩት ወ/ ማርያም
18- የሴቶችና ህጻናት ጉዳዮች ሚኒስትር - ወ/ ሮ ደሚቱ ሃምቢሣ
19- የወጣቶች ስፖርት ሚኒስትር - አቶ ርስቱ ይርዳው
20- ለገቢዎችና ጉምሩክ መስሪያ ቤት ኃላፊ ሚኒስትር - አቶ ከበደ ጫኔ
21- ለመንግስት ኮሚኒኬሽን ጉዳዮች ጽ/ ቤት ኃላፊ ሚኒስትር - ዶ/ ር ነገሪ ሌንጮ
በነበሩበት የቀጠሉ ሚኒስትሮች
•    1- ም/ ጠቅላይ ሚኒስትር - አቶ ደመቀ መኮንን
2- የመከላከያ ሚኒስትር - ሲራጅ ፈርጌሣ
3- የፌደራልና አርብቶ አደር ጉዳዮች ሚኒስትር - አቶ ካሣ ተ/ብርሃን
4- የፌደራል ጠቅላይ አቃቤ ህግ - አቶ ጌታቸው አምባዬ
5- የመገናኛ ኢንፎርሜሽን ቴክኖሎጂ ሚኒስትር - ዶ/ ር ደብረጽዮን ገ/ሚካኤል
6- የኢንዱስትሪ ሚኒስቴር - አቶ አህመድ አብተው
7- የሰራተኛ ማህበራዊ ጉዳይ ሚኒስትር - አቶ አብዱልፈታህ አብዱላሂ
8- የብሔራዊ ኘላን ኮሚሽን ኃላፊ ሚኒስትር - ዶ/ ር ይናገር ደሴ
9- የመንግስት ተጠሪ ዋና ሚኒስትር - አቶ አስመላሽ ወ/ ስላሴ

 የታዋቂው ሰዓሊ ሰይፉ አበበ ከ50 በላይ ስዕሎች ለእይታ የሚቀርብበት “Think Out Side  the Box” የተሰኘ የሥዕል አውደ ርዕይ፣ ዛሬ ከቀኑ 10፡00 ላፍቶ ሞል በሚገኘው ላፍቶ አርት ጋለሪ ይከፈታል፡፡
ለቀጣዩ አንድ ወር ለተመልካች ክፍት ሆኖ በሚቆየው በዚህ አውደ ርዕይ ለእይታ የሚቀርቡት ስዕሎች፡- የመልክአ ምድርን፣ መልክአ ሰማይንና አጠቃላይ የተፈጥሮን ውበትና ቀለም የሚያሳዩ በ3D እና 2D የተዘጋጁ ስራዎች እንደሆኑ ሰዓሊው ለአዲስ አድማስ ገልጿል፡፡ ከዚህ ቀደም ከሌሎች ሰዓሊዎች ጋር በውጭና በአገር ውስጥ ለበርካታ ጊዜያት ሥራዎቹን በቡድን ለዕይታ ያቀረበው ሰዓሊው፤ ለብቻው ደግሞ በጣይቱ ሆቴል፣. በብሔራዊ ሙዚየም፣ በብሔራዊ ቴአትር አርት ጋለሪና በዓለም ጋለሪ ሥዕሎቹን ለተመልካች አቅርቧል፡፡ ሰዓሊ ሰይፉ በ1987 ዓ.ም ከአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ፣ አለ ፈለገ ሰላም የስነ ጥበብና ዲዛይን ት/ቤት የተመረቀ ሲሆን በአሁን ሰዓት ከስዕል ስራው በተጨማሪ በካክተስ የሚዘጋጀው የ“what’s out” መፅሄት ግራፊክስ ዲዛይነርና የኢትዮጵያ ሰዓሊያንና ቀራፂያን ማህበር ዋና ፀሐፊ በመሆን እያገለገለ ይገኛል፡፡

 አዶት ሲኒማና ቲያትር፤ አዳዲስ የሆሊውድ ፊልሞችን ከዛሬ ጀምሮ ለተመልካች እንደሚያሳይ ተገለጸ፡፡ ከሁለት ዓመታት በፊት በ30 ሚሊዮን ብር ወጪ ተገንብቶ ቲያትሮችንና የአማርኛ ፊልሞችን ለተመልካቾች ሲያቀርብ የቆየው ሲኒማ ቤቱ፤ አዳዲስ የሆሊውድ ፊልሞችን በማምጣት ማሳየት እንደሚጀምር የአዶት ሲኒማ ሥራ አስኪያጅ አቶ ዘለዓለም ብርሃኑ ለአዲስ አድማስ ተናግረዋል፡፡ በሆሊውድ የተሰሩና የተመረጡ አዳዲስ ፊልሞችን ከሆሊውድ እኩል ለማሳየት ዝግጅቱን አጠናቋል ብለዋል - ሥራ አስኪያጁ፡፡  

   - የምርጫ ውጤትን እቅጩን የሚገምቱት ፕሮፌሰር፣ ትራምፕ ያሸንፋል ብለዋል
                   - ሪፐብሊካኑ ኮሊን ፖል ድምጻቸውን የሚሰጡት ለዲሞክራቷ ሄላሪ እንደሆነ አስታውቀዋል

        የሳምንታት ጊዜ በቀረው የአሜሪካ ፕሬዚዳንታዊ ምርጫ ሪፐብሊካኑን ወክለው የሚወዳደሩት አነጋጋሪው ዕጩ ዶናልድ ትራምፕ፣ 3ኛው የዓለም ጦርነት የሚጀመረው ተፎካካሪያቸው ሄላሪ ክሊንተን ይዛው በተነሳቺው የውጭ ጉዳይ ፖሊሲ ሳቢያ ነው ሲሉ ተናገሩ፡፡
ሄላሪ ክሊንተን በሶርያ ጉዳይ ላይ የያዘቺው እቅድ በአሜሪካና በሩስያ መካከል የከፋ ግጭት የሚያስከትልና ለሶስተኛው የዓለም ጦርነት መነሻ ሊሆን አንደሚችል ትራምፕ ባለፈው ማክሰኞ ባደረጉት ቃለ ምልልስ ማስጠንቀቃቸውን ዘ ኢንዲፔንደንት ዘግቧል፡፡
የሄላሪን ዕቅድ በመደገፍ በምርጫው ድምጻችንን የምንሰጣት ከሆነ፣ ሶስተኛው የዓለም ጦርነት መጀመሩ አይቀሬ ነው ያሉት ትራምፕ፤ ሄላሪ ስታብጠለጥለው ከከረመቺው ከሩስያው ፕሬዚዳንት ቭላድሚር ፑቲን ጋር ለመደራደር ያላት ብቃት እንደሚያጠራጥራቸው በመግለጽ፣ በሁለቱ አገራት መካከል ያለውን ግንኙነት ታበላሸዋለች ብለዋል፡፡
ያልተለመዱ ክስተቶች የተስተናገዱበት የዘንድሮው የአሜሪካ ፕሬዚዳንታዊ ምርጫ ቅስቀሳ እየተጧጧፈ ወደ መጨረሻው ምዕራፍ በደረሰበት በአሁኑ ወቅት፣ ሪፐብሊካኑ የቀድሞው የአሜሪካ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ኮሊን ፖል ዲሞክራቷን ሄላሪን እንደሚመርጡ ማስታወቃቸውን የዘገበው ደግሞ ስካይ ኒውስ ነው፡፡ ሊዲሞክራቷ ዕጩ ድምጻቸውን እንደሚሰጡ በይፋ የሚናገሩ ስመጥር ሪፐብሊካኖች እየተበራከቱ መምጣታቸውን የጠቆመው ዘገባው፣ ኮሊን ፖልም ሄላሪ እንደ አገር መሪ ያላትን የካበተ ልምድና ክህሎት በማድነቅ ድምጻቸውን ለእሷ እንደሚሰጡ ባለፈው ማክሰኞ ማስታወቃቸውን ገልጧል፡፡
በተያያዘ ዜና ምንም እንኳን በርካታ ቅድመ ትንበያዎች በቀጣዩ ምርጫ ዲሞክራቷ ሄላሪ በለስ እንደሚቀናት እያመላከቱ ቢሆንም፣ የአሜሪካን ምርጫ ውጤት በመተንበይ የሚታወቁት የፖለቲካ ተንታኙ ፕሮፌሰር ሄልሙት ኖርፖዝ ግን፣ በስተመጨረሻ ድል የትራምፕ ትሆናለች ሲሉ መተንበያቸውን ዘ ኢንዲፔንደንት ዘግቧል፡፡
ላለፉት 100 ያህል አመታት በአሜሪካ ከተከናወኑ ፕሬዚዳንታዊ ምርጫዎች ከአንዱ በቀር የሁሉንም ውጤት በትክክል የገመቱት የኒውዮርኩ ሰኒ ስቶኒ ብሩክ ዩኒቨርሲቲ መምህር ፕሮፌሰር ሄልሙት ኖርፖዝ፣ በቀጣዩ ምርጫ ትራምፕ እንደሚያሸንፉ በይፋ ተንብየዋል፡፡
ፕሮፌሰር ኖርፖዝ የፈጠሩትና ያለፈውንና የወደፊቱን የፕሬዚዳንታዊ ምርጫ ውጤት የሚያመላክተው የትንበያ ቀመር፣ እ.ኤ.አ ከ1912 አንስቶ በተደረጉት የአገሪቱ ምርጫዎች ላይ ያቀረበው ትንበያ ከአንዱ በስተቀር በሁሉም ስኬታማ እንደነበር የጠቆመው ዘገባው፣ ቀመራቸውን ተጠቅመው የሰጡት ትንበያ ያልያዘላቸው እ.ኤ.አ በ2000 በተካሄደው ምርጫ ብቻ እንደነበርም አስታውሷል፡፡