Administrator

Administrator

በመምህር ሃይማኖት ታደሰ አራጋው የተፃፈው “ያንዳንድ አጥንት እጣ” የተሰኘ የግጥም መድበል በገበያ ላይ ዋለ፡፡ በመፅሃፉ ውስጥ ተካተቱት ግጥሞች ማህበራዊና ፖለቲካዊ እንዲሁም ፍልስፍናዊ ጉዳዮችን ያነሳሉ ተብሏል፡፡ 43 ግጥሞችን የያዘው መድበሉ፤ 48 ገፆች ያሉት ሲሆን በ20 ብር እየተሸጠ እንደሆነ ታውቋል፡፡
ደራሲው ከዚህ ቀደም “እንበለ ጥበብ” እና “የማርገዝ ነፃነት” የተሰኙ የግጥም መፅሃፍት ያሳተመ ሲሆን ከሌሎች ገጣሚያን ጋር በመሆንም “የማለዳ ነፍሶች” የተሰኘ የግጥም መድበል ለአንባቢያን አድርሷል፡፡

“ድህረ አብዮት ሰልፍ ሜዳ ለሁለት ተከፍሎ፣ ቀበሌ ሃያ ዘጠኝና ቀበሌ ሰላሳ ተብሎ ተዋቀረ፡፡ ሰልፍ ሜዳ

የሚለው ስም የመጣውም ከአብዮቱ በኋላ ነው፡፡ ነዋሪዎቹ ለሁሉ ነገር ይሰለፉ ነበር፡፡ ለዳቦ፣ ለጋዝ/ኪሮሲን፣

ለስኳር፣ ለዘይት፣ ለዱቤ ዱቄት፣ ለቦኖ ውሃ፣ የዕድር ሊቀመንበር ለመምረጥ… ሰልፍ….ሰልፍ….ሰልፍ ለሁሉም፡፡ …

የአሜሪካ ኢምፔሪያሊዝም ተስፋፊነትን ለማውገዝ፤ ለላቲን አሜሪካ ወዛደሮች ትግል አጋርነትን ለማሳየት፤… ነጋ

ጠባ፤ ዘመን መጣ፤ ዘመን … ሔደ… ሰልፍ! ሰልፍ! ሰልፍ! ሰልፍ! ነው! የሌላ ሠፈር ሰዎች፤ ሰልፍ እኛ ሰፈር ብቻ

ያለ ይመስል፤ “ሰልፍ ሜዳ” ሲሉ ጠሩት መንደራችንን፡፡ … እኛም የሰልፍ ሜዳ ልጆች ሆንን፡፡



ንዋይ ንዋይ የሚሸቱ የጥበብ ስራዎችን ዱካ ለማነፍነፍ ብዙ መድከም አይጠበቅብንም፡፡ በልባሳቸው መዥጎርጎር

አሊያም በሚመርጧቸው ርዕሶች በቀላሉ እንለያቸዋለን፡፡ ስገምት ነጋዴ ጸሐፍት ከመጽሐፍት ገበያ ትኩሳት ጋር

አብሮ ከፍ ዝቅ የሚል ርዕስና ርዕሰ-ጉዳይ ሲቃርሙ የሚውሉ ይመስለኛል፡፡ ስገምት ንግዱንም ትርፉንም

በሚገባ ያውቁበታል፡፡ ስገምት ቴሌቪዥን ማታ ማታ “ስግብግብ ነጋዴዎች…” ብሎ ዜና ባነበበ ቁጥር የሚበረግጉ

ይመስለኛል፡፡ ሁልጊዜም የሚከፋኝ ግን አንባቢ እነዚህን ንዋይ አፍቃሪ ጸሐፍት ፊት አለመንሳቱ ነው፡፡
ጥበበኛስ? ጥበበኛ ከነጋዴ ፀሐፍት ጋር ሆድና ጀርባ ነው፡፡ በገበያው ግርግር ውስጥ ተላላነት ያጠቃዋል፡፡

ትርፍና ንግድ በሚሉት ጉዳዮች ባይተዋርነቱ ያይላል፡፡ ተመስጦ ውስጥ ሆኖ በጥቂቶች ልብ ይበራል፡፡ ጥበበኛ

ቅድሚያ የሚሰጠው ለህሊናው ነፃነት ነው፡፡ ቅድምያ የሚሰጠው ለራሱ ስሜት ነው - ለመንፈሱ፡፡
ጥበበኛ ጥበብን ሲከውን እንደመተንፈስ ይቀለዋል፡፡ ዘና ማለቱ ለተደራሲያኑም ይተርፋል፡፡ በዚህ መሰሉ

መዝናናት የተበጃጀ የምናብ አብራክ ክፋይን አይቶ እንዳላየ ማለፍ ከባድ ነው፡፡ እኔም ከሰሞኑ ከአራሙቻው

መሐል ጎንበስ ቀና የሚል እሸት ጥበብ፣ ከዓይኔ ሲገባ ዝምታን ወግድ ብዬ አንድ ሁለት ለማለት ፈለግሁ፡፡

ለትችትም ለሙገሳም የሚበቃ ንፁህ የጥበብ ሥራ ማግኘት አሁን አሁን እንደመታደል የሚቆጠር ሆኗል፡፡ ሰልፍ

ሜዳ ከእነዚህ ውስጥ የሚካተት የጥበብ ሥራ ነው፡፡ በዚህ ፅሁፌ ይሄን ልቦለድ ነው ለአንባቢያን ለማስቃኘት

የወደድኩት፡፡
የሰልፍ ሜዳ ሽፋን፤ ጽልመት የወረሰው፣ የኾነ የሚጨፈግግ  ቀንን የሚያስታውስ ነው፡፡ ጫፉ የማይታይ ጉም

የለበሰ ሰማይ ስር፣ ከሰው የተራቆተ ጎዳና፣ በደብዛዛ ብርሃን አንዲት ወልጋዳ ሰማያዊ ታክሲ እንደነገሩ

ትታያለች፡፡ ደራሲው ግርማ ተስፋው፤ ተደራሲያኑ ገና የመጽሐፉን ልባስ ማየት ሲጀምሩ በፈተና ሊቀበላቸው

የፈለገ ይመስላል፡፡ እንዴት? ቢሉ በመጽሐፉ ሽፋን ላይ የድብርት ቆሌ አርብቦበታልና ነው፡፡
የመጽሐፍ ሽፋን የጎጆ በር ማለት ናት፡፡ ደራሲው ከመጽሐፉ ገጾች ሳቅና ጨዋታን እንዳንጠብቅ ጎጆዋን ከል

አልብሷታል፡፡ በ240 ገጾች የተቀነበበው ይህ ረዥም ልብወለድ፤ መቼቱ በደርግ መውደቂያ ዋዜማ ላይ ነው፡፡

መላ ታሪኩ ተጀምሮ የሚጠናቀቀው አዲሳባ ከምትገኝና ደራሲው በምናብ ከፈጠራት “ሰልፍ ሜዳ” ከተባለች

መንደር (ሰፈር) ነው፡፡ ይህ ምናባዊ ሰፈር “ሰልፍ ሜዳ” ለምን ተባለ ለምንል ተደራሲያን በገጽ 70 ላይ እንዲህ

ተብራርቶልናል፡-
“ድህረ አብዮት ሰልፍ ሜዳ ለሁለት ተከፍሎ፣ ቀበሌ ሃያ ዘጠኝና ቀበሌ ሰላሳ ተብሎ ተዋቀረ፡፡ ሰልፍ ሜዳ

የሚለው ስም የመጣውም ከአብዮቱ በኋላ ነው፡፡ ነዋሪዎቹ ለሁሉ ነገር ይሰለፉ ነበር፡፡ ለዳቦ፣ ለጋዝ/ኪሮሲን፣

ለስኳር፣ ለዘይት፣ ለዱቤ ዱቄት፣ ለቦኖ ውሃ፣ የዕድር ሊቀመንበር ለመምረጥ… ሰልፍ….ሰልፍ….ሰልፍ ለሁሉም፡፡ …

የአሜሪካ ኢምፔሪያሊዝም ተስፋፊነትን ለማውገዝ፤ ለላቲን አሜሪካ ወዛደሮች ትግል አጋርነትን ለማሳየት፤… ነጋ

ጠባ፤ ዘመን መጣ፤ ዘመን … ሔደ… ሰልፍ! ሰልፍ! ሰልፍ! ሰልፍ! ነው! የሌላ ሠፈር ሰዎች፤ ሰልፍ እኛ ሰፈር ብቻ

ያለ ይመስል፤ “ሰልፍ ሜዳ” ሲሉ ጠሩት መንደራችንን፡፡ … እኛም የሰልፍ ሜዳ ልጆች ሆንን፡፡
በዚህ ማብራሪያ ደራሲው የሰልፋም ሰፈርነቱን (ሰሙን ማለት ነው) ያትት እንጂ ወርቁን ሊነግረን አልዳዳውም፡፡

ወርቁን ገጽ በገፋን ቁጥር፣ እንደ በቆሎ እየፈለፈልን እንድናገኘው ነው የፈለገው፡፡
ሰልፍ ሜዳ ዙሪያ ጥምጥም ነው፡፡ ወሰን ድንበር ፍጻሜው አይታየንም፡፡ ወትሮ እንደለመድናቸው የልብወለድ

ታሪኮች፣ የስሜት ከፍታን በእያንዳንዱ ኩርባ ላይ ለመቃረም ከዳዳን አይሳካልንም፡፡ እፍ ክንፍ ያለ የፍቅር

ታሪክ፣ ሴራ ጉንጎና፣ ልብ ሰቀላና የመሳሰሉት የሥነ-ፅሁፍ ጌጦች በዚህ መጽሀፍ ውስጥ ብርቅ ናቸው፡፡ ለልብ

ሰቀላ ሲሉ መጽሐፍ ለሚያነቡ ተደራሲያን፣ ይህ መጽሐፍ ደመኛቸው ቢኾን አይገርምም፡፡ በሰልፍ ሜዳ ኩርባ

የሚባል ነገር የለም፡፡ የታሪክ መቋጫ ፍለጋ ከተንደረደርን፣አድማስ ጋር ሰዶ ማሳደድ እንገባለን፡፡
የመፅሐፉ አንኳር ጭብጦች
መጽሐፉ ስለብቸኝነት፣ ስለባዶነት፣ ስለከንቱነት----መብሰክሰክ ይበዛዋል፡፡ ገጸ-ባህርያቱ እዚህ ግቡ የማይባሉ

ተራ ሰዎች ናቸው፡፡ እንደ ወይዘሮ ከድጃ አይነት ቡና ማፍያ የሚለምኑ፤ እንደ እሙ ከሴተኛ አዳሪ ተወልደው

ቆሎ የሚያዞሩ… ወዘተ፡፡ እንዲያውም አንዳንዶቹ ሲኖሩ ትዝ የማይሉን፣ ነገር ግን ሲሞቱ ይበልጥ

የምናስታውሳቸው ናቸው፡፡ ለምሳሌ ንጉሴ የተባለው ገጸ ባህሪ ወፍጮ አስፈጪ ነው፡፡ የሰልፍ ሜዳ ሰው፣ ንጉሴ

በህይወት መኖሩ ትዝ ያለው ለአካባቢው ዳቦ በምታድል መኪና የተገጨ ዕለት ነው፡፡ “… ንጉሴ ሰው ሳይሆን

የሰው ጥላ ይመስለኝ ነበር፤ በኑሮው ሳይኾን በሞቱ ሰው መስሎ ተሰማኝ” (ገጽ 8)፡፡
በገመናችን የሚዘባበቱት አያቱ!
“ስማ የእግዜር ቀልድ ይሉኝ ነበር አያቴ” በሚል ንግግሩ ነው የልቦለዱን ዋና ገፀ ባህሪ የምንተዋወቀው፡፡ ታሪኩ

ይባላል፡፡ በአንደኛ መደብ ሙሉ ታሪኩን የሚተርክልን ይኼ ገጸ ባህሪ ነው፡፡ የታሪኩ አያት ብርቱ ሰብእና

አላቸው፡፡ ብሽቀታቸውን መሸሸግ አይሆንላቸውም፡፡ በአገኙት አጋጣሚ ፈጣሪን በነገር ጎሸም ማድረግ

ይቀናቸዋል፡፡ ማህበረሰቡንም እንደዚያው፡፡ ጉሸማው ለሌላ አይደለም፡፡ የንቃ ዓይነት ደውል ነው፡፡
አዛውንቱ በገመናችን ይዘባበታሉ፡፡ በአመለካከታችን፣ በስንፈታችን፣ በጉብዝናችን፣ በእምነታችን፣ በክህደታችንና

በታሪካችን ላይ ክፉኛ ይሳለቃሉ፡፡ እኝህ አዛውንት የደራሲውን የብሽቀት ጥሪት ጠቅልለው የተሸከሙ

ይመስላሉ፡፡ በፈጣሪም በህብረተሰቡም ተሳላቂው አያት፤ ጣሊያንን ያንቀጠቀጡ ጎበዝ አርበኛ ነበሩ፡፡ ኋላ ላይ  

ወራሪው ኃይል ከሀገር ሲባረር፣ ወደ ጭቃ ረጋጭነት ሥራ ተሸጋገሩ፡፡ እርሳቸው በዱር በገደሉ ሲዋደቁ ግን

ባንዳዎች የፋሺስት ጫማ ይወልውሉ ነበር፡፡ ከድል በኋላ ጫማ ወልዋዮቹ ባንዳዎች ሹመት ሲሰጣቸው፣

እርሳቸው ግን ጭቃ ረጋጭ ሆነው ቁጭ አሉ፡፡
“ሀገሬ ኢትዮጵያ ሞኝ ነሽ ተላላ፤
የሞተልሽ ቀርቶ የገደለሽ በላ፡፡” የሚለውን ስንኝ ያስታውሰናል - የእሳቸው ታሪክ፡፡
የታሪኩ አያት ታሪክ ብቻ መርምረው አያበቁም፡፡ ስነልቦናችንን ይሰልላሉ፡፡  
የታሪኩ አያት ቄስ ቢኾኑም በአንድ አጋጣሚ ከታሪክ ጋር ሆነው በ “መታፈሪያ ጠጅ ቤት” ታድመዋል፡፡ የሰልፍ

ሜዳ “ጉልቤ” ተስፋሁን፤ አንድ ቦርጫም ጠጪን አንበርክኮ፣ እላዩ ላይ ጠጅ እያፈሰሰ ይንከተከታል፤

ይሳለቅበታል፤ ያዋርደዋል፡፡ ሰዎች በጉልቤው ተስፋሁን፣ እርር ድብን ቢሉም ማንም ለመናገር አይደፍርም፡፡

በሁኔታው የተናደዱ የሚመሰሉት ሽማግሌው የታሪኩ አያት፤ ከተቀመጡበት ብድግ ብለው ጉልቤው ተስፋሁንን

በቁጣ ገደሉት ሲባል፣ በተቃራኒው የተንበረከከውን ሰውዬ ከተስፋሁን ጋር ተደርበው መደብደብ ያዙ፡፡ ይበልጥ

የምንደመመው ግን ይህን ያደረጉበትን ምክንያት ሲገልጹ ነው፡፡ በገጽ 67 እና 68 ላይ እንዲህ ይላሉ፡-
“… መንበርከክ እንደ ተስቦ ከሰው ሰው እንደሚጋባ አታውቅም? አናት አናቱን ማለትማ ተንበርካኪውን ነው!

ኧ---- ያኔ ነው ሰው የሚኾነው፡፡”
“ተንበርካኪ መቼ ምክንያት ያጣል፤ብትጠይቀው እኖር ብዬ፤ ልጅ አሳድግ ብዬ ይልኻል፡፡ የሰው ዝቃጭ፡፡ የኖረ

መስሎታል፡፡ ሞት አይቀር! ተረጋጭም የረጋጭን ያህል ጥፋተኛ ነው፡፡… ይበለው”
ጭቆናን አሜን ብሎ የሚኖር ሰብእና፣ የሀጢያት ዳፋው ከጨቋኙ በላይ ይገዝፍብናል፡፡ ተንበርካኪነትና ጎብጦ

የሚያዘግም ስነልቦናን ደራሲው እንዲህ ባለ ተራ የጠጅ ቤት ግጭት ሊያስዳስሰን ሲሞክር እንወደዋለን፤ እናም

አበጀህ እንለዋለን፡፡
አብደላ ሻይ ቤት እንደ ብሶት አደባባይ
ሳምቡሳ የሚጠበስበት ሻይ ቤት፣ በሰልፍ ሜዳ ላይ ታሪክን ለማንጎድ መደላደያውን ያመቻቸ ታንኳ ሆኖ

እናገኘዋለን፡፡ አብደላ ሻይ ቤት፣ የመጣው ሁሉ ብሶቱን የሚጥልበት ጉሮኖ ነው፡፡ ደራሲው ይህንን ስፍራ

በዋነኛነት ለመጠቀም የፈለገው ምን አልባትም ለአብዛኛው ህብረተሰብ ቅርብ የሆነ ስሜትን እፈጥርበታለሁ

በሚል ምናባዊ ጥንስስ ተገፋፍቶ ሊሆን ይችላል፡፡ በአብደላ ሻይ ቤት ታሪክ ይወጣል ይወርዳል፡፡ ፍልስፍናን

በላይ በላይ እንመገባለን፡፡ ተፈላሳፊዎቹ ደሞ ማንም በማይገምተው መልኩ የመጀመሪያ ደረጃ መምህራን

ናቸው፡፡ አብዮት ተስፋ በሚባል ትምህርት ቤት ያስተምራሉ፡፡ አንባቢው እንዴት ይህን የመሰለ ጥልቅ

ፍልስፍናን ከመጀመሪያ ደረጃ መምህራን እናገኛለን? ብሎ ቢሞግት አይፈረድበትም፡፡ የጊዜ ስሌት ግን ሙግቱን

ውሃ እንዳይቋጥር ያደርገዋል፡፡ ተፈላሳፊዎቹ መምህራን ከአብዮቱ ግርግር ዘመን በፊት ነው የበቀሉት፡፡

መምህራኑ የደራሲው ምናባዊ ፈጠራ ቢኾኑም በዘመኑ የነበሩትን ታሪካዊ ኩነቶች እያነሱ የሚጥሉበት የአስተሳሰብ

ጥልቀት፣ የገሃዱ ዓለም አካል አድርገን እንድንቆጥራቸው ያስገድደናል፡፡ በዚህም ምክንያት የሰልፍ ሜዳ

መምህራንን ከአሁን ዘመን መምህራን ጋር ለማነፃፀር ልኬት ውስጥ የምንገባባቸው አጋጣሚዎች ይበራከቱብናል፡፡
የሁለት መንትዮች ወግ
መንትዮቹ ቸርነትና አሸናፊ ይባላሉ፡፡ የታሪኩ የልብ ጓደኛ የለዓለም ወንድሞች ናቸው፡፡ ደራሲው የሁለቱን

መንትያዎች ስነልቦና የታሪካችን ማሳያ አድርጎ ቀርጾታል፡፡ እዚህ ጋ የደራሲውን ታሪክ አዋቂነት ልብ ይሏል፡፡

ቸርነት በአብዮቱ ዘመን አካባቢ የበቀሉ ልሂቃንን ይወክላል፡፡ ከታሪክ እንደምንረዳው፣ በአብዮቱ መባቻ ላይ

በፊት አውራሪነት የተሰለፉት ልሂቃን ስነልቦና ወጥ ነበር፡፡ ሁሉም፣ ጽንፈኝነትን ያነገቡ፣ ሁሉም እውቀትን

ሳይፈትሹ እንደወረደ የሚያጠልቁ ደብተራዎች ነበሩ፡፡ የቸርነትን ግልብ ስነልቦና በዘመኑ በነበሩት ዘውግ-ዘለል

የፖለቲካ ድርጅቶች ላይ እናገኘዋለን፡፡ ቸርነትን ስንመለከት የማርክሲዝም ሌኒንዝምን ጥቅስ በቃል በማነብነብ

ብቻ ለአዋቂነታቸው ሚዛን የሚሰፍሩ ምሁራንን እናስታውሳለን፡፡ ቸርነት በማርክሲዝም ሌኒንዝም ከተጠመቀ

በኋላ፣የቤተሰቡን እምነት በአንዲት ጀምበር ለመናድ የሚጣደፍበት ሁኔታ ሀገራችንን ከድጡ ወደ ማጡ

የሰደዷትን የአብዮቱን ዘመን የፖለቲካ ልሂቃን ያስታውሰናል፡፡ ለቸርነት ጽንፈኝነት ማሳያ መንትያ ወንድሙ

አሸናፊ በተቃራኒው ተስሏል፡፡ አሸናፊ ሚዛናዊ ነው፡፡ አማካይ ስፍራን መያዝ ይወዳል፡፡ የአርስቶትልን “Golden

Mean”  እዚህ ጋ እናስታውሳለን፡፡ “ዘ ጎልደን ሚን” አርስቶትል ሚዛናዊነትንና ክፍት ስነልቦናን የገለጸበት

መጠሪያ ነው፡፡ በእርግጥም አሸናፊ ይህ ስያሜ ይገባዋል፡፡
ጉዱ ካሳዊው - ለዓለም
ለዓለም መኩሪያ የደራሲው የምናብ ከፍታ ውላጅ ነው፡፡ በ“ፍቅር እስከ መቃብር” ከግርግሩ መሐል

በባይተዋርነት ቆሞ የሚሟገተውን ጉድ ካሳን በሰልፍ ሜዳ ላይ ለዓለም ሆኖ እናገኘዋለን፡፡ ለዓለም ለእንቶ

ፈንቶው ፊት መንሳት ያውቅበታል፡፡ እጅግ የላቀ ቁርጠኝነትንና ጽናትን ከሚጠይቁ ጉዳዮች ጋር ሲጋፈጥ

እናስተውለዋለን፡፡ በገጽ 104፤ ለዓለም ከጓደኛው ታሪኩ ጋር በሚያደርገው ምልልስ የአመለካከቱን አስኳል

እናገኛለን፡-
“መፍራት ካለብህ ብቻውን መሆን የማይወድን ሰው ፍራ፡፡ ሰው በህብረት ሲሆን እምነት የለኝም፡፡ ታሪኩ፤ ሰው

ማህበራዊ እንስሳ ነው የሚሉህን አትስማቸው፡፡ ቆፈናሞች!! አፍንጫችሁን ላሱ በላቸው፡፡ በቡድን አደራጅተው፤

ከፋፍለው ከፋፍለው ለማጋደል፣ ለማሰርና ለመግዛት እንዲመቻቸው ነው፡፡ ሰው ብቸኛ እንስሳ ነው፡፡ ትልቁ

ትራጄዲ ብቸኝነቱን መሸሹና መፍራቱ ነው፡፡”
ይህ ዓይነቱ ከመንጋ የመነጠል አባዜ፣ የጉዱ ካሳ እምነትና አመለካከት፣ ቀኖና ውላጅ ነው፡፡ ለዓለም ግርግሩን

ለመሸሽ በሚያደርገው ጥረት፣ ከህዝበ ሰልፍ ሜዳ ብርቱ ወከባ ሲያጋጥመው እናስተውላለን፡፡
የመጽሐፉ ድክመቶች
ገጸ ባህሪን ከማስተዋወቅ አንጻር
ገፀ-ባህሪን ከተደራሲያኑ ጋር ከማስተዋወቅ አንጻር በመፅሃፉ ውስጥ ጉልህ ክፍተት ይታያል፡፡ በመጀመሪያው

ምዕራፍ መግቢያ አካባቢ፣ በመኪና አደጋ ለህልፈተ ህይወት የበቃው ንጉሴ፤ ድንገት ሞትን እንደ አልአዛር ድል

አድርጎ፣ በገጽ 93 በዳቦ ሰልፍ ላይ እናገኘዋለን፡፡ የንጉሴ ከአንባቢው ጋር ድንገት ፊት ለፊት መላተም፣ የታሪኩን

ፍሰት ያንገራግጨዋል፡፡ ስለንጉሴ ምንነት በቅጡ ለማወቅ ንባቤን ገታ አድርጌ፣ ያለፍኳቸውን ገጾች እንደገና

መመርመር ነበረብኝ፡፡ ይህ ግርታ የኔ ብቻ ሳይሆን የብዙ ተደራሲያን እንደሚሆን እገምታለሁ፡፡
መቼት
ገፀ-ባህሪያቱ በጊዜና በቦታ መለኪያ ሲሰፈሩ በደንብ አልታሹም፡፡ አብደላ ሻይ ቤት በልብወለዱ ውስጥ

በጉልህነት ከሚነሱት ቦታዎች አንዱ ነው፡፡
በገጽ 11 ላይ፤ “አብደላ በቀይ ሽብር ዘመን በተባራሪ ጥይት የተገደለ የሙሰማ ታናሽ ወንድም ነው፤ በተባራሪ

ጥይት ለሞተ፣ ሐውልት የሚያቆምም የሚያጀግንም ስለሌለ፣ ይህን ምግብ ቤት በታናሽ ወንድሙ ስም ጠራው፤

የአብደላ ስምም በመላው ሰልፍ ሜዳና በዙሪያው ባሉ የአዲስ አበባ ሰፈሮች ሁሉ ታወቀ” ሲል ስለስያሜው

ያትታል፡፡
ደራሲው ስያሜው ከጊዜው ጋር ይጣጣም አይጣጣም ግድ የሰጠው አይመስልም፡፡ በቀይ ሽብር የተገደለን

ሰው፣በአዲስ አበባ ነዋሪዎች ፊት ለመዘከር ድኅረ ደርግና ቅድመ ደርግ ለየቅል መሆናቸውን ማንም ሊረዳው

የሚችል ሀቅ ነው፡፡ ሌላው ቢቀር በቀበሌ ሹማምንት ዘንድ ይህ ተግባር ጥርስ የሚያስገባ ድፍረት ነው፡፡ ለዚህም

እራሱን ልብወለዱን ምስክር ማድረግ እንችላለን፡፡ ደራሲው የሰልፍ ሜዳ ህብረተሰብ የቀበሌውን ሊቀመንበር

ጓድ እንዳይላሉ መርሻን ሲመለከት፣ ብርክ እንደሚይዘው በመጀመሪያው ምዕራፍ ገጾች ላይ እየደጋገመ

እየነገረን፣ ሙሰማን እንደ ጸረ አብዮት በሚያስቆጥር ተግባር ላይ ደፋር ማድረጉ ከምን የመጣ ነው ብለን

እንድንጠይቅ ያስገድደናል፡፡ እዚህ ጋ ከግምት መጣፍ ያለብን የቤቱን ጭርንቁስነት ሳይሆን የጊዜውን እውነታ

ነው፡፡ በወቅቱ የነበረው የፖለቲካ ትኩሳት፣ የቤቱ ስያሜን ተዓማኒነት እንደሚያጎድል መታሰብ ነበረበት፡፡
በእንግዳ ቃላት ማደናገር
ሰልፍ ሜዳ የቃላት ደሃ አይደለም፡፡ የቃላት ደሃ አለመሆኑ ግን ያዘናጋው ይመስላል፡፡ ደራሲው እንግዳ ቃላትን

ወይም አገላለጽን ያለ ማብራሪያ ዝም ብሎ ነው የሚያልፉቸው፡፡ ለአብነት ያህል በገጽ 175 ላይ እንዲህ የሚል

ስንኝ ሰፍሯል፡-
ቀነውኒ አደውየ ወእገርየ
ወኈለቍ ኩሉ አዕፀምትየ
ቀነውኑ እንደውየ ወአገርየ
ትንሽ አለፍ ብሎ “አምንስቲቲ ሙክርያ” የሚል ቃል ይገኛል፡፡ ደራሲው የቃላቱን  ትርጉም በቅንፍ ጠቆም

አድርጎ ማለፍ ወይም የህዳግ ማጣቀሻ መጠቀም ይችል ነበር፡፡
በአጠቃላይ ግን ሰልፍ ሜዳ ባልተሄደበት ጎዳና ለመንጎድ የጀገነ፣ ግሩም የቋንቋ ዉበት ያለው፣ እንደወቅቱ

በድፍረት ተነስቶ ስለማያውቁት ጉዳይ መጽሐፍ የመጻፍ ደዌ ዉስጥ ያልተዘፈቀ፣ በስክነትና በእውቀት የተከተበ፣

ኩልል ያለ የጥበብ ስራ ሆኖ አግኝቼዋለሁ፡፡ ደራሲው አንድ ተጨማሪ የጥበብ ስራ ከደገመን ምናልባት አዳም

ረታ ታናሽ የጥበብ ወንድም አገኘ ብለን ለማወጅ እንደፍር ይሆናል፡፡  

በበለጠ በላቸው ይሁን የተፃፈው “ጅቡቲ የጥገኝነታችን መስፈሪያ” የተሰኘ መጽሐፍ ባሳለፍነው ሳምንት መጨረሻ

ለንባብ በቃ፡፡ በስድስት ምዕራፎች ተከፋፍሎ በ222 ገፆች የተመጠነው መጽሐፉ፤ ከአፄ ኃይለስላሴ መንግስት

ጀምሮ በበርካታ የኢትዮጵያና ጅቡቲ ጉዳዮች ላይ ትንታኔ ያቀርባል፡፡ መጽሐፉ በ65 ብር ለገበያ እንደቀረበ

ለማወቅ ተችሏል፡፡

ላቭሊ የውበት ስራ ማሰልጠኛ ተቋም በተለያዩ የውበት ሥራ ሙያዎች ያሰለጠናቸውን ተማሪዎች በሚቀጥለው ሳምንት ቅዳሜ ከቀኑ 6፡00 ሰዓት ጀምሮ በግሎባል ሆቴል እንደሚያስመርቅ ስራ አስኪያጁ አቶ ፋሲል ሚካኤል አስታወቁ፡፡ በእለቱ የሚመረቁት ተማሪዎች በሞዴሊንግ፣ በፀጉርና በውበት ስራ፣ በፋሽን ሾው፣ እንዲሁም በሌሎች የፈጠራ ስራዎች የሚሰጠውን ትምህርት ተከታትለው ያጠናቀቁ ሲሆን በየዘርፉ በትምህርት ብቃታቸው ብልጫ ላሳዩ ተማሪዎች ሽልማት እንደሚሰጥም ዋና ስራ አስኪያጁ ተናግረዋል፡፡ ላቭሊ የውበት ማሰልጠኛ ተቋም ላለፉት 16 ዓመታት በዘርፉ ስልጠና ሲሰጥ የቆየ ሲሆን በርካታ ዜጐችን የሙያ ባለቤት እንዳደረገም ተገልጿል፡፡

ውድ እግዚአብሔር፡-
ት/ቤት ሁሉም የራሱ ምርጥ ጓደኛ አለው፤ እኔ ብቻ ነኝ የራሴ ጓደኛ የሌለኝ፡፡ አንድ ጓደኛ ልትሰጠኝ ትችላለህ?

ግን ቶሎ ብለህ እሺ?!
ዴቭ - የ6 ዓመት ህፃን
ውድ እግዚአብሔር፡-
ሃና ከክፍላችን በጣም ቆንጆ ናት፡፡ ሳሚ ደግሞ በሩጫ የሚበልጠው የለም፡፡ ቲና ጥርሷ ያምራል፡፡ ለእኔ ግን

ምንም የተለየ ነገር አልሰጠኸኝም፡፡ ረስተኸው ነው?
ጁዲ - የ6 ዓመት ህፃን
ውድ እግዚአብሔር፡-
እህቴ ባል እንድታገባ እባክህ ቆንጆ አድርጋት፡፡
ቤቲ - የ7 ዓመት ህፃን
ውድ እግዚአብሔር፡-
የፕላስቲክ አበቦች ስታይ አትናደድም? እኔ አንተን ብሆን በጣም ነበር የምናደደው፡፡
ጆሲ - የ8 ዓመት ህፃን
ውድ እግዚአብሔር፡-
ታላቅ ወንድሜ እኔን እንደሚቆጣኝ፣ እኔም የምቆጣው ወንድም እፈልጋለሁ፡፡ ትንሽዬ ወንድም ትሰጠኛለህ?
ቶኒ - የ6 ዓመት ህፃን
ውድ እግዚአብሔር፡-
ሶፊ የሚያምር ጫማ አላት፡፡ እኔም የእሷ ዓይነት ጫማ እፈልጋለሁ፤ ግን ልሰርቃት አልፈለግሁም፡፡ አንተ

ልትሰጠኝ ትችላለህ?
ውድ እግዚአብሔር፡-
አንዳንዴ ጥርሴን የውሸት ስቦርሽ ታውቅብኛለህ አይደል? ግን ለማሚ እንዳትነግርብኝ እሺ!?
ካሌብ - የ5 ዓመት ህፃን
ውድ እግዚአብሔር፡-
ከዓለም ላይ መጥፎ ነገሮችን ካላስወገድክ በሚቀጥለው ጊዜ የምትመረጥ አይመስለኝም፡፡ እኔ እኮ ላንተ ብዬ

ነው፡፡ ወይስ መመረጥ አትፈልግም?
ኤርሚ - የ7 ዓመት ህፃን
ውድ እግዚአብሔር፡-
ከፃፍካቸው ታሪኮች ሁሉ የወደድኩት የኖህን ታሪክ ነው፡፡ እኔም በውሃ ላይ መጓዝ ደስ ይለኛል፡፡
ሳቤላ - የ8 ዓመት ህፃን




Monday, 29 September 2014 08:40

የፍቅር ጥግ

ዝነኞች ስለጋብቻ የዛሬዋ ምሽት እጅግ ልዩ ናት፡፡ በፓሪስ የኤፍል ማማ ጫፍ ላይ ቃል ኪዳናችንን ዳግም ማደሳችን ምን ያህል እፁብ ድንቅ እንደሆነ ልገልፀው አልችልም፡፡ ማሪያ ኬሪ (አሜሪካዊት ዘፋኝ) ምንም ዓይነት ሁኔታ ቢገጥመን ተደጋግፈን ማለፋችን ጠቅሞናል፡፡ ጃዳን የመሰለች ሴት በማግኘቴ ዕድለኛ ነኝ፡፡ እጅግ ግሩም ሴት፣ ሚስትና እናት ናት፡፡ ዊል ስሚዝ (አሜሪካዊ የፊልም ተዋናይ) ህፃናቱ እንድንጋባ ጫና አሳድረውብናል፡፡ የእኛ መጋባት ለእነሱ ምን ማለት እንደሆነ አልተገነዘብንም ነበር፡፡ ስንጋባ ግን ለእኛም ያለውን ትርጉም ተረድተነዋል፡፡ ብራድ ፒት (አሜሪካዊ የፊልም ተዋናይ) አሁንም ልክ መጀመሪያ ላይ ስንተዋወቅ እንደነበረው እንፋቀራለን፤ ዕፁብ ድንቅ የሆኑ ልጆች አሉን … በጣም ደስተኞች ነን፡፡ የስራና የቤተሰብ ኃላፊነታችንን በማመጣጠን ህይወታችንን እንመራለን፡፡ ምንጊዜም ቅድምያ የምንሰጠው ለልጆቻችን ነው፡፡ ዴቪድ ቤክሃም (እንግሊዛዊ የእግር ኳስ ተጫዋች) ከ20 ዓመት በፊት ልታገባኝ የተስማማችው እቺ ሴት ባትኖር፣ ዛሬ የሆንኩትን አይነት ሰው አልሆንም ነበር፡፡ ይሄን ነገር በአደባባይ ልበለው፡- ሚሼል፤ እንዲህ አፍቅሬሽ አላውቅም፡፡ መላው የአሜሪካ ህዝብ በቀዳማዊት እመቤትነትሽ በፍቅር ሲወድቅልሽ እንደማየት የሚያኮራኝ ነገር የለም፡፡ ባራክ ኦባማ (የአሜሪካ ፕሬዚዳንት) ጋብቻ የሰመረ እንዲሆን ሁለት ነገሮች ያስፈልጋሉ፡፡ አንደኛው ለስኬታማነቱ መትጋት ነው፡፡ ሌላው ከእናንተ በላይ የሆነ ሰው ማግባት ነው፡፡ እኔ በሁለቱም ረገድ ተሳክቶልኛል፡፡ ቤን አፍሌክ (አሜሪካዊ የፊልም ተዋናይ) በእኔና በእሷ ግንኙነት ውስጥ ሁለት መመሪያዎች አሉን፡፡ የመጀመሪያው መመሪያ፤ ማናቸውንም ነገሮች እያገኘች እንደሆነ እንድታስብ ማድረግ ነው፡፡ ሁለተኛው መመሪያ ደግሞ፤ ማናቸውንም ነገሮች በራሷ መንገድ እንድታከናውን መፍቀድ ነው፡፡ ይሄ አሁን ድረስ እየሰራልን ነው፡፡ ጀስቲን ቲምበርሌክ (እንግሊዛዊ ዘፋኝ)

Monday, 29 September 2014 08:33

ገጣሚያን ስለህይወት


* ህይወት ስዕል መስራት እንጂ ሂሳብ ማስላት     አይደለም፡፡
ኦሊቨር ዌንዴል ሆልምስ
* ህይወት ፈፅሞ እውን ለማይሆን ነገር የሚደረግ ረዥም ዝግጅት ነው፡፡
ዊሊያም በትለር ይትስ
* ነፃነት የሌለው ህይወት መንፈስ እንደሌለው ገላ ነው፡፡
ካህሊል ጂብራን
* ፍቅር የሌለው ህይወት አበባ ወይም ፍሬ እንደሌለው ዛፍ ነው፡፡
ካህሊል ጂብራን
* ህይወት ራሱ ጥቅስ ነው፡፡
ጆርጅ ሉይስ ቦርግስ
* ህይወት የተገነባው የሰው ልጅ ቀኑን ሙሉ ከሚያስባቸው ሃሳቦች ነው፡፡
ራልፍ ዋልዶ ኤመርሰን
* በ80 ዓመታችን ተወልደን ቀስ እያልን ወደ 18 ብንጠጋ ኖሮ፣ ህይወት በእጅጉ በደስታ የተሞላ ይሆን ነበር፡፡
ማርክ ትዌይን
*ህይወት የምንቆጥበው ሳይሆን የምንጠቀምበት ንብረታችን ነው፡፡
ዴቪድ ኸርበርት ሎውረንስ

* በትምህርት ቤትና በህይወት መካከል ያለው ልዩነት ምንድን ነው? ትምህርት ቤት፤ ትምህርት ትማርና ለፈተና

ትቀርባለህ፡፡ በህይወት ውስጥ ግን በቅድሚያ ትምህርት የምታገኝበት ፈተና ነው የሚሰጥህ፡፡
ቶም ቦዴት
* ላጣኸው ነገር ሁሉ ሌላ ነገር አግኝተሃል፤ ለምታገኘው ነገር ሁሉ ሌላ ነገር ታጣለህ፡፡
ራልፍ ዋልዶ ኤመርሰን
* በየቀኑ የምንከፍታቸውና የምንዘጋቸው      በሮች፣ የምንኖረውን ህይወት ይወስኑታል፡፡
ፍሎራ ዊትሞር

              የፅንስ ማቋረጥ ሕግ አተረገጓጎም... 551(ሀ) ‹‹በመደፈር ወይም በዘመድ መካከል በተደረገ የግብረ ሥጋ ግንኙነት ምክንያት ፅንሱ የተገኘ ሲሆን...›› የፅንሱ መቋረጥ የሚካሄደው እርጉዟ ሴት በምትሰጠው ቃል መነሻ መሰረት ነው፤ “ከአስገድዶ መድፈር ፣ ከቤተዘመድ ጋር በተደረገ ግንኙነት ምክንያት”.. ማለቷ በቂ ይሆናል፡፡ ሌላ ተጨማሪ ማብራሪያ ወይም ማስረጃ መስጠት አይጠበቅባትም፡፡ ይህም ቃሏ በሴትየዋ የህክምና ካርድ ላይ ይመዘገባል፡፡ 552 (ለ) የእርግዝናው መቀጠል በእናቲቱም ሆነ በፅንሱ ህይወት ወይም በእናቲቱ ጤንነት ላይ አደጋ የሚያስከትል ሲሆን ወይም የልጁ መወለድ በእናቲቱ ጤንነት ህይወት ላይ አደጋ የሚያመጣ ሲሆን.. 551(ሐ) “ፅንሱ ሊድን የማይችል ከባድ የአካል ጉድለት (deformed) ያለው ሲሆን” የጤና ባለሙያው አስፈላጊውን ምርመራ አድርጎ የማይድን የአካል ወይም የህብለዘር ጉድለት (genetic deformity) በፅንሱ ላይ ከታየ የፅንስ ማቋረጥ ሊካሄድ ይችላል፡፡

551 (መ) “አንዲት እርጉዝ ሴት የአካል ወይም የአእምሮ ጉዳት ያለባት በመሆኑ ወይም ለአካለ መጠን ያልደረሰች በመሆኗ የሚወለደውን ህፃን ለማሳደግ የህሊናም ሆነ የአካል ዝግጅት የሌላት ሲሆን” 551 (2) በፍጥነት በሚደረግ ህክምና ካልሆነ በስተቀር ሊወገድ የማይቻል ከባድና ጊዜ የማይሰጥ አደጋ ሲያጋጥም በህጉ አስገዳጅ ሁኔተ ተብሎ ስለሚቆጠር ..አንቀፅ 75.. ፅንስ ማቋረጥ አያስቀጣም፡፡ በአንቀፅ 551(2) በተደነገገው ሁኔታውስጥ ሆነው ለሚመጡ ሴቶች የፅንስ ማቋረጥ ተግባር ለመፈፀም ፈቃድ የተሰጣቸው ሁሉ በፍጥነት የፅንስ ማቋረጡን አገልግሎት መስጠት አለባቸው፡፡ የኢፊድሪ ጤና ጥበቃ ሚኒስ..ር ሰኔ 1998 አዲስ አበባ ደህንነቱ ያልተጠበቀ ጽንስ መቋረጥን በሚመለከት ባለፈው እትም ለንባብ ያልነው ቀጣይ ይሆናል በዚህ አምድ የምናስነብባችሁ፡፡

ምንጮቻችን ዶ/ር ደመቀ ደስታ በአይፓስ ኢትዮጵያ ሲኒየር አድቫይዘር ፣ዶ/ር ጌትነት በቀለ ከበርጌስ ክሊኒክ ባለቤትና የህክምና ባለሙያ ከተክለ ሀይማኖት ጠቅላላ ሆስፒታል ሲ/ር ነጻነት አባተ እና ሲ/ር አበባ ስለሺ ከበርጌስ ክሊኒክ ናቸው፡፡ እንደ ዶ/ር ደመቀ ማብራሪያ የአገልግሎቱ አሰጣጥ ልዩነት አለው ፡፡ “...የከተማና የገጠሩ ህዝብ በተለይ ደግሞ ወጣቶች በሚሰባሰቡባቸው ቦታዎች እና ሌላውን አካባቢ በምናነፃፅርበት ጊዜ ልዩነት አለው፡ ከተማ ውስጥ በተለይ የወጣቱ ክፍል ለስራ ፍለጋም፣ ከትምህርትም ጋር በተያያዘ ከገጠሩ ክፍል የሚመጡ ሲሆን እውቀቱና ግንዛቤው እንዲሁም አገልግሎቱም ስለማይኖር ብዙዎቹ ላልተፈለገ እርግዝና የተጋለጡ ናቸው ፡፡ ለምሳሌም ትልልቅ ኮንስትራክሽን የሚካሄድባቸው አካባቢዎች፣ ትልልቅ የእርሻ ጣቢያዎች በተለይም የአበባ እርሻ ያለባቸው አካባቢዎች እና ዩኒቨርስቲዎች ፣ ኮሌጆች ያሉባቸው አካባቢዎች የወጣቶች መሰባሰቢያዎች ሲሆኑ ፋሲሊቲዎቻችንን በምናይበት ጊዜ በቂ አገልግሎት እየሰጠን ነው ማለት አይቻልም፡፡ የገጠሩን የህብረተሰብ ክፍል በምናይበት ጊዜ ቁጥሩ አነስ ቢልም ለተጠቃሚዎች የተቻለውን ያህል አገልግሎት እየተሰጠ ይገኛል፡፡ ተጠቃሚዎች አልጋ በመያዝም ይሁን ሙያተኛን ከመጋራት አንጻር ምን ያህል የህክምናው አሰራር ላይ ጫና ይፈጥራሉ? ለሚለው ሀሳብ ሲ/ር ነጻነት ከተክለሀይማኖት ጠቅላላ ሆስፒታል የሚከተለውን ገልጣለች፡፡

“...ደህንነቱ የተጠበቀ ጽንስ ማቋረጥ አገልግሎት የሚሰጣቸው ተጠቃሚዎች እንደሌላ ሕመምተኛ አልጋ አይይዙም ፡፡ እንደዚህ አይነት እናቶች ተስተናግደው ብዙም ሳይቆዩ የሚሸኙ ናቸው፡፡ ዋናው ነገር የምናየው ከጽንስ ማቋረጥ በሁዋላ የሚሰጣቸውን የምክር አገልግሎት ነው፡፡ ስለቤተሰብ ምጣኔ እዛው ትምህርቱ ይጀመርላቸዋል ፡፡ ሌላው ነገር የእሷን ህይወት አደጋ ላይ የሚጥለውን ደም መፍሰስ ቆሟል ወይንስ አልቆመም የሚለውን ክትትል ማድረግ ነው ፡፡ ስለዚህ ከጽንስ ማቋረጥ በኋላ ያለውን ደም መፍሰስ እንዲሁም ከጽንስ ማቋረጥ በሁዋላ ያለው መመረዝ.. ሽቃሶስሰ..ሽቄቃ .. መኖር አለመኖር በተወሰኑ ሰአታት ከተረጋገጠ በበሁዋላ ወደ ቤትዋ እንድትሔድና በተሰጣት ቀጠሮ መሰረት እንድትታይ ትደረጋለች፡፡ ሲስተር አበባ ከበርጌስ ባስተላፈችው ምክር አዘል መልእክት... “.. የቤተሰብ ምጣኔ አገልግሎትን ሴቶች በተቻለ መጠን ተጠቃሚ ቢሆኑ ጥሩ ነው፡፡ ደህንነቱ የተጠበቀ ጽንድ የማቋረጥ አገልግሎት በምንሰጥበት ጊዜ እግረ መንገዳችንን ስለቤተሰብ ምጣኔ አገልግት ምክር እንሰጣለን፡፡ የጽንስ ማቋረጥ አገልግሎቱን ምንም እንኩዋን ሕጉ በሚፈቅደው መሰረት ብንሰራውም አገልግሎት ፈላጊዋን ለመርዳት ሲባል እንጂ ደስ የማይል ነገር አለው፡፡

ነገር ግን ግዴታ ስለሆነ ደስ ባይለንም ስራውን እንሰራለን፡፡ ሴቶች አስቀድሞውኑ ያልተፈለገ እርግዝናን ቢከላከሉ ግን ጽንስ የማቋረጥ አገልግሎትን ፈልገው አይመጡም ነበር ፡፡” ሕጉ በሚፈቅደው መሰረት ደህንነቱ የተጠበቀ ጽንስ ማቋረጥ በትክክል ተግባር ላይ ውሎአልን? ለሚለው ዶ/ር ጌትነት በቀለ ከበርጌስ እንደሚሉት... .....ምንድነው ...ቀረ የምንለው ነገር ...በተለይ በመንግስት ተቋሞች ዙሪያ አንዳንድ ችግሮች ይታዩኛል፡፡ ለምሳሌ ...ለእኛ ቅርብ የሆኑ የመንግስት ጤና ጣቢያዎች፣ክሊኒኮችጋ ሊታዩ የሄዱ ሴቶች አንዳንድ ጊዜ ወደክሊኒንችን ይመጣሉ፡፡ ለምን ወደዚህ መጣችሁ? ተብለው ሲጠየቁ የተለያየ መልስ ይሰጣሉ፡፡ በእኛ በኩል ከአይፓስም ይሁን ከሜሪስቶፕስ የሚሰጠንን ድጋፍ በትክክል በመጠቀም ፣ለባለሙያዎች የሚሰጡ የተግባር ስልጠናዎችም ስለሚያግዙን አገልግሎቱን እንሰጣለን፡፡ ነገር ግን ማንኛውም የህክምና ተቋም ጥያቄውን በትክክል ተቀብሎ ቢያስተናግድ መልካም ነው፡፡ በወደፊቱ አሰራርም መንግስትም የበለጠ ትኩረት ሰጥቶት አሁን እየሰራን ያለነው ደህንነቱ የተጠበቀ ጽንስ ማቋረጥ በቤተሰብ ጤና አገልግሎት እየተተካ የሚሄድበትን እና ሴቶችም በዚህ ምክንያት ጉዳት እንዳይደርስባቸው ሁኔታው ወደተሻሻለ ደረጃ ቢመጣ ጥሩ ነው፡፡ አገልግሎት አሰጣጡን በተመለከተ ዶ/ር ደመቀ ከአይፓስ እንደሚሉት... “...በተፈለገው መልኩ ሁሉም የጤና ተቋማት ይህን አገልግሎት እየሰጡ ነው ማለት አይቻልም፡፡ በአብዛኛው ስራውን የሚሰሩት ድጋፍ የሚሰጣቸው የጤና ተቋማት ናቸው ፡፡ ስለዚህ በተቻለ አቅም አገልግሎቱ ለሁሉም የህብረተሰቡ ክፍል ተደራሽ ሚሆንበት መንገድ መመቻቸት አለበት ፡፡

ኢትዮጵያ ውስጥ በአሁን ጊዜ ወደ ሶስት ሺህ ሁለት መቶ እና ከዛ በላይ ጤና ተቋማት ቢኖሩም አገልግሎት እየሰጡ ያሉት ግን ምናልባት ቢበዛ ቢበዛ ከአንድ ሺህ ሁለት መቶ ወይንም ከአንድ ሺህ ሶስት መቶ የሚበልጡ አይደሉም፡፡ ስለዚህ ደህንነቱን የተጠበቀ ፅንስ ማቋረጥ ለህብረተሰቡ ለሁሉም ተደራሽ እንዲሆን ሁሉም ፋሲሊቲዎች ላይ በሁሉም የጤና ተቋማት አገልግሎት ቢኖር እና ግንዛቤውን አስመልክቶ ህብረተሰቡ ምን ያህል ያውቃል የሚለውን መፈተሸ ያስፈልጋል፡፡ ዶ/ር ጌትነት በቀለ በስተመጨረሻ በሰጡት አስተያየት “...በአገልግሎት አሰጣጣችን በተለይም ደም እየፈሰሳት የምትመጣ ሴት ካጋጠመችን እስዋን ሳንረዳ ወደቤታችን አንሄድም፡፡ ይህ እንግዲህ እናቶች ደህንነቱ ባልተጠበቀ ጽንስ ማቋረጥ ምክንያት ጉዳት እንዳይደርስባቸው የተቻለንን ለማድረግ ነው፡፡ ይህ አሰራር እርግጠኛ ባልሆንም በሌሎችም የሚተገበር ይመስለኛል፡፡ ከዚህ በተጨማሪም ብዙ ሴቶች ገንዘብ ሳይኖራቸው ይህ ችግር ስለሚገጥማቸው ክሊኒኩ በተቻለ መጠን ሁኔታውን እያየ በያዙት ገንዘብ ሳያጨናንቃቸው አገልግሎቱን እየሰጠ ይኛል፡፡

እስዊፍት የሚባል በጎ አድራጊ ድርጅት የጎዳና ልጆች እርዱልኝ እያለ ሲያመጣ የምንቀበል ሲሆን እንዲያውም በሳምንት ሶስት ሰው በነጻ እንዲታከሙ ፈቅደናል፡፡ለዚህ በተላያየ ቦታ ያሉ በዚህ ጉዳይ ችግር የሚገጥማቸው ሰዎች ካሉ እና ይህንን መልእክት የሰሙ መጥተው ቢያናግሩን አቅማችንን ባገናዘበ መልኩ የነፃ አገልግሎት ለመስጠት የበኩላችንን ጥረት እናደርጋለን፡፡ ዶ/ር ደመቀ ደስታ በስተመጨረሻ እንደገለጹት እንደ ውጭው አቆጣጠር በ2008/ የተጠና ጥናት እንደሚያሳየው ደህንነቱ ያልተጠበቀ ጽንስ ማቋረጥ ለአጠቃላይ የእናቶች ሞት የሚያስከትለው አስተዋፆ ወደ ዘጠኝ ኀ ነው፡፡ በአሀኑ ጊዜም ሌላ ሰፋ ያለ ጥናት በአገር ደረጃ ማለትም በአይፓስ ኢትዮጵያ ፣ጤና ጥበቃ ሚኒስ..ር ፣የኢትዮጵያ የጽንስና ማህጸን ሐኪሞች ማህበ ESOG Ethiopian Public Health Association እየተሰራ ሲሆን ይህ ጥናት ሲያልቅ በትክክል በአሁን ወቅት ደህንነቱ ያልተጠበቀ ጽንስ ማቋረጥ ለእናቶች ሞት ያለውን አስተዋጽኦ ለማወቅ ያስችላል፡፡

           ዓለምአቀፉ ማህበረሰብ ለምዕራብ አፍሪካ ቀውስ ፈጣን ምላሽ ካልሰጠ፣ የኢቦላ ወረርሽኝ ተጠቂዎች ቁጥር እስከመጪው ጥር ወር አጋማሽ 1.4 ሚ. ሊደርስ እንደሚችል የአሜሪካ የበሽታ ቁጥጥር ማዕከል ተነበየ፡፡ ሰዎች በከፍተኛ ፍጥነት በኢቦላ እየተጠቁ እንደሆነ የጠቆመው ማዕከሉ፤ እስካሁን በቫይረሱ ተጠቅተዋል ተብሎ ከተነገረው በ2.5 እጅ የሚልቁ ተጠቂዎች እንዳሉ ሰሞኑን ባወጣው ሪፖርት ገልጿል፡፡

በቅርቡ የተጀመረው ዓለምአቀፍ እርዳታ ከቀጠለ ግን ይሄ አስከፊ ሁኔታ ሊቀለብስ ይችላል ብለዋል - የአሜሪካ የበሽታ ቁጥጥር ማዕከል ዳይሬክተር ቶም ፍሪይዴን፤ ሰሞኑን ለጋዜጠኞች በሰጡት መግለጫ፡፡ የዓለም ጤና ድርጅት ባወጣው ሪፖርት መሰረት፤ በምዕራብ አፍሪካ 5800 የሚገመቱ ሰዎች በበሽታው የተጠቁ ሲሆን ከ2800 በላይ ሞተዋል፡፡ የአሜሪካ የበሽታ መቆጣጠሪያ ማዕከል አዲሱ ሞዴል፤ የገዳዩን ቫይረስ ስርጭት ለመከላከል የኢቦላ በሽተኞችን ከጤነኞች መነጠል ባለው ፋይዳ ላይ ያተኩራል፡፡

እስካሁን የኢቦላ ተጠቂዎች ቁጥር በሁለቱ አገራት በየ20 ቀኑ በእጥፍ እየጨመረ እንደሆነ የጠቆመው ማዕከሉ፤ ለዚህም ምክንያቱ በበሽታው የተያዙ ሰዎች ከጤነኞች ጋር ባላቸው ንክኪ በቫይረሱ ስለሚበክሏቸው ነው ብሏል፡፡ ከአስሩ የኢቦላ በሽተኞች ሰባቱ በቤታቸው ወይም በህክምና ማዕከል ውስጥ ተነጥለው እንዲቀመጡ ቢደረጉ፣ በላይቤሪያና በሴራሊዮን ያለው ወረርሽኝ በጥር ወር አጋማሽ ላይ ሊገታ እንደሚችል ተጠቁሟል፡፡

የአሜሪካ የበሽታ መቆጣጠሪያ ማዕከል፣ የመከላከያ ኃይል እንዲሁም ዩኤስኤይድ በምዕራብ አፍሪካ ገንዘብና የሰው ሃይላቸውን እያፈሰሱ ሲሆን የተባበሩት መንግስታት ድርጅትና ሌሎች አገራትም የዚ ጥረት አካል እንደሆኑ የፕሁሬዚዳንት ባራክ ኦባማ ልዩ ረዳትና የብሔራዊ ደህንነት ም/ቤት ከፍተኛ ዳይሬክተር ጋይሌ ስሚዝ ተናግረዋል፡፡ ከቅርብ ሳምንታት ወዲህ ዓለምአቀፍ የእርዳታ ጥረቶች እየጨመሩ ቢመጡም፤ ቫይረሱ ግን ስርጭቱን ቀጥሏል ያለው አሶሼትድ ፕሬስ፤ ከችግሮቹ አንዱ በበሽታው ክፉኛ በተጠቁት ጊኒ፣ ላይቤሪያና ሴራሊዮን በቂ የሆስፒታል አልጋዎች እንዲሁም የጤና ሰራተኞች፣ ወይም ሳሙናና ውሃ ሳይቀር አለመኖሩ ነው ብሏል፡፡

            ሥራዬን ላጣ እችላለሁ የሚል ስጋትና ጭንቀት በአስም የመያዝ አደጋን ሊጨምር እንደሚችል በአውሮፓ የተደረገ አዲስ ጥናት አመለከተ፡፡ ጥናቱ በጀርመን የሚገኙ ከ7ሺ በላይ ተቀጣሪ ሠራተኞችን ያሳተፈ እንደነበር ታውቋል፡፡ እነዚህ ተሳታፊዎች አውሮፓ የኢኮኖሚ ድቀት ባጋጠማት ወቅት (እ.ኤ.አ ከ2009 እስከ 2011 ዓ.ም) ስለመተንፈሻ አካላት መዛባትና በሁለት ዓመት ውስጥ ከሥራችን እንፈናቀላለን ብለው ያስቡ እንደሆነ ተጠይቀው መልስ ሰጥተዋል፡፡ ጥናቱ በተካሄደባቸው ጊዜያት ከተሳታፊዎቹ ውስጥ ከ100 በላይ የሚሆኑት አዲስ የአስም በሽታ እንደተቀሰቀሰባቸው ኸልዝዴይ ኒውስ ጥናቱን ጠቅሶ ዘግቧል፡፡ ከሥራ ጋር የተገናኘ ጭንቀት በ25 በመቶ ባደገ ቁጥርም በአስም የመያዝ አደጋ በ24 በመቶ እንደጨመረ ተመራማሪዎቹ ጠቁመዋል፡፡

ሥራ የማጣት ዕድላችን ከፍተኛ ነው ብለው ያስቡ የነበሩት ተሳታፊዎችም በአስም የመያዝ ዕድላቸው ወደ 60 በመቶ ማሻቀቡን ጥናቱ ጠቁሟል፡፡በሁለት ዓመት ውስጥ ሥራችንን የማጣት ዕድላችን ዝቅተኛ ነው ወይም ስጋት የለብንም ካሉት ይልቅ ሥራ የማጣት ዕድላችን ከፍተኛ ነው ያሉት በዕድሜ ወጣት፣ በትምህርት ብዙ ያልገፉ፣ ያላገቡና ዝቅተኛ ወርሃዊ ደሞዝ ያላቸው እንደነበሩ ተመራማሪዎቹ ገልፀዋል፡፡ የስራ ማጣት ያሰጋቸው ተሳታፊዎች፤ ቋሚ የሥራ ኮንትራት የማግኘት ዕድላቸው እጅግ ዝቅተኛና በድብርት ለመሰቃየት የበለጠ የተጋለጡ እንደነበርም ጥናቱ ይጠቁማል፡፡ የጥናት ውጤቱ ባለፈው ሳምንት “ጆርናል ኦፍ ኢፒዲሞሎጂ ኤንድ ኮሙኒቲ ኸልዝ” ላይ እንደወጣ ተገልጿል፡፡

ጥናቱ፤ ከስራ ጋር የተያያዘ ጭንቀት ለአስም መንስኤ እንደሆነ አላረጋገጠም ይላሉ - ተመራማሪዎቹ፡፡ ነገር ግን ቀደም ሲል በስነልቦና ጭንቀት ላይ የተደረገ ጥናትም ለአስም አደጋ የሚያጋልጥ ምክንያት ሊሆን እንደሚችል ደርሰንበታል ብለዋል፡፡ “የጥናት ውጤቱ፤ በኢኮኖሚ ድቀቱ ወቅት ጊዜ በእንግሊዝ የመተንፈሻ አካላት መዛባት በከፍተኛ ሁኔታ የጨመረበትን ምክንያትም ሊመልስ ይችላል” በማለት ተመራማሪዎቹ በጆርናሉ ጋዜጣዊ መግለጫ ላይ አስፍረዋል፡፡ ይሄ በዚህ እንዳለ የአባቶች አጫሺነት ህፃናትን ለአስም በሽታ እንደሚያጋልጥ በጀርመን የተካሄደ ጥናት ጠቁሟል፡፡ በተለይ አባት የረዥም ጊዜ አጫሽ ከሆነ፣ ህፃኑ በአስም የመያዝ ዕድሉ በከፍተኛ ደረጃ ይጨምራል ብለዋል - አጥኚዎቹ፡፡ ቀደም ሲል የአባት ማጨስ በህፃኑ ላይ ስለሚያስከትለው አሉታዊ ተፅዕኖ ማንም ትኩረት ሰጥቶት እንደማያውቅ ያወሱት ተመራማሪዎቹ፤ አዲሱ ጥናት የእናትየዋን ያህል አባትም በልጅ ጤና ላይ ይሄን ያህል ተፅዕኖ እንደሚያሳርፍ መታወቁ ጠቃሚ ነው ብለዋል፡፡