Administrator

Administrator

በአነስተኛ ካፒታል በኢንጂነር ፀደቀ ይሁኔ  ተመስርቶ ከ30  አመታት በላይ በኮንስትራክሽንና በሪልእስቴት ዘርፍ ጉልህ ሥራዎችን እያከናወነ የሚገኘው ፍሊንትስቶን ኢንጅነሪንግ ፤ ከሃምሌ 1 ቀን 2015 ዓ.ም ጀምሮ አክሲዮኖቹን ለህዝብ ክፍት በሆነ ገበያ ለሽያጭ እንደሚያቀርብ አስታወቀ፡፡   
ኩባንያው ይህን ያስታወቀው ባለፈው ማክሰኞ፣ ግንቦት 8 ቀን 2015 ዓ.ም፣  በሃያት ሪጀንሲ  በሰጠው ጋዜጣዊ መግለጫ  ነው፡፡
የኩባንያው መሥራችና ባለቤት ኢንጂነር ፀደቀ ይሁኔ የአክሲዮን ሽያጩን ለመጀመር ያስፈለገበትን ምክንያት ሲያስረዱ፤ “ፍሊንትስቶን ኢንጅነሪንግ ላለፉት ሰላሳ ዓመታት በግለሰብ ደረጃ ተመሥርቶ በሺዎች የሚቆጠሩ ቤቶችን በመገንባት ለተጠቃሚዎች ማድረስ ከቻለ፣ በሺዎች የሚቆጠሩ ባለአክሲዮኖችን በውስጡ ቢይዝ በመቶ ሺዎች የሚቆጠሩ ቤቶችን ለመገንባት ይችላል።” የሚል እሳቤን መነሻ ማድረጋቸውን  ገልጸዋል።
10 ሚሊዮን አክሲዮኖች ለሽያጭ መዘጋጀታቸው የተገለጸ ሲሆን፤ የአንድ አክሲዮን ዋጋ አንድ ሺህ ብር ሆኖ የአክሲዮን ባለቤትነቱ ከ20 ሺህ ብር የማያንስና ከሁለት ሚሊዮን ብር የማይበልጥ እንደሚሆን ተጠቁሟል፡፡
ለሽያጭ የቀረበው አነስተኛ የአክሲዮን መጠን ዝቅተኛው 20 ሺህ ብር፣ ከፍተኛው ደግሞ ሁለት ሚሊዮን ብር የተደረገበትን ምክንያት በተመለከተ  የኩባንያው ዋና ሥራ አስኪያጅ አቶ ሞገስ ማቲያስ ሲያስረዱ፤ ከፍተኛ የገንዘብና የዕውቀት አቅምን በመገንባት መካከለኛ ገቢ ካላቸው ደንበኞች ጀምሮ ብዙኃኑን ተጠቃሚ የሚያደርግ የሕዝብ ኩባንያን ለመፍጠር በማሰብ መሆኑን ተናግረዋል።
የአክሲዮን ገዢዎች ለአክሲዮኑ ያዋሉት ገንዘብ በቀጣይ ለቤት መግዣነት ማዋል ቢፈልጉ፤ በማንኛውም ጊዜ ኩባንያው አክሲዮናቸውን ገዝቶ፣ ያላቸውን ገንዘብ በካሬ ሜትር በማስላት የቤት ባለቤት የሚሆኑበት ሥርዓት መዘርጋቱም ተገልጧል፡፡የግል ድርጅቶችን ለህዝብ ክፍት በሆነ ገበያ ማቅረብ ሁለት ቁልፍና ተመጋጋቢ ፋይዳ እንደሚያስገኝ የተጠቆመ ሲሆን፤ አንደኛው ከፍተኛ የገንዘብና የዕውቀት አቅም ማምጣቱ ነው፤ ሁለተኛው  ደግሞ ተጠያቂነትንና ግልጽነትን በማስፈን መልካም የኮርፖሬት አስተዳደርን  ያሰፍናል ተብሏል፡፡
ከተቋቋመበት ከ1984 ዓ.ም ጀምሮ በመላ ሃገሪቱ በልዩ ልዩ የመሰረተ ልማት ግንባታ ሥራ ተቋራጭነት ሲንቀሳቀስ ቆይቶ ከአስራአምስት ዓመታት በፊት ወደ ቤቶች ልማት ገበያ የተቀላቀለው ፍሊንትስቶን ሆምስ፤ በትምህርት፣ በውሃ፣ በመብራት ሃይል፣ በመንገድና በመንግስት የቁጠባ ቤቶች ፕሮጀክቶች ላይ ግዙፍ አሻራዎችን ማኖሩ ታውቋል፡፡
ወደ ሪልእስቴት ከተቀላቀለ በኋላ ባሉት አስራአምስት ዓመታትም በሺህ የሚቆጠሩ ደንበኞችን የቤት ባለቤቶች ማድረጉ ተጠቁሟል፡፡
“ሁሌም በለውጥ ሰዓት ለባለሃብቶች ሦስት ነገሮች የመሆን ዕድል ያጋጥማል፤ ቆዛሚም፣ አዝጋሚም፣ ተምዘግዛጊም መሆን ይቻላል፡፡ እንደ ንግድ ድርጅት ተምዘግዛጊ መሆኑ ግን እጅጉን ያዋጣል፤ ሀገራችንን በጋራ፣ ሀብታችንን በአክሲዮን እንገንባ” ብሏል፤ፍሊንትስቶን ሆምስ በመግለጫው፡፡


 በዲኤምጂ ኢቨንትስና በአገር በቀሉ ኢቲኤል ኢቨንትስ ኤንድ ኮሚዩኒኬሽን ትብብር የተዘጋጀውና ለ3 ቀናት የዘለቀው የቢግ 5 ኮንስትራክት ኢትዮጵያ ኤግዚቢሽን ዛሬ ይጠናቀቃል፡፡
በግንባታው ዘርፍ የተሰማሩ አለማቀፍና አገር በቀል ኩባንያዎች የሚሳተፉበት ይኸው ከግንቦት 10 ቀን 2015 ጀምሮ እስከ ዛሬ ለ3 ቀናት ክፍት ሆኖ የቆየው ኤግዚቢሽኑ፤ በዘርፉ ያሉ እድሎችንና አማራጮችን በመጠቆም በዘርፉ የተሰማሩ ግብአት አቅራቢዎች በተለያዩ ግዙፍ ግንባታዎች ላይ ተሳትፎ እንዲያደርጉና የራሳቸውን አሻራ እንዲያኖሩ ምቹ እድሎችን ፈጥሯል ተብሏል፡፡ ከ24 የአለማችን አገራት የተውጣጡ ከ140 በላይ የኤግዚቢሽን አቅራቢዎች የተሳተፉበት ይኸው ኤግዚቢሽን፤ በከተማና መሰረተ ልማት ሚኒስቴርና በኢትዮጵያ ኮንስትራክሽን ስራዎች ኮርፖሬሽን ዕውቅናና ድጋፍ ተደርጎለታል፡፡በሚሊኒየም አዳራሽ የተካሄደውና በቆየው ኢግዝቢሽን ላይ ከ6ሺ በላይ የህንፃ ንድፍና ግንባታ ስራ ላይ የተሰማሩ ባለሙያዎች፣ የህንፃ ጥገናና የንብረት አስተዳደር ባለሙያዎችና እጅግ ተፅዕኖ ፈጣሪ ከሆኑ የዘርፉ አካላት እና ልሂቃን ጋር በአንድ መድረክ ለመገናኘት ያስቻለም ነው፡፡ ቢግ 5 በመካከለኛው ምስራቅና በአፍሪካ በግንባታ እንዱስትሪ ውስጥ ከአራት አስርት አመታት በላይ ግንባር ቀደም ሆኖ ቆይቷል፡፡
ቢግ 5 ኮንስትራክት፤ ኢትዮጵያ የሀገር ውስጥና የውጪ ኩባንያዎች ሙያዊ ክህሎታቸውንና እውቀታቸውን ለኢትዮጵያ የግንባታ እንዱስትሪ የሚያሳዩበት ሁነኛ መንገድ እንደሆነም በዚሁ ጊዜ ተገልጿል፡፡


 ሕብረት ባንክ፤ የቴክኖሎጂ የእውቀት ሽግግርና ልምድን ማካፈል በሚቻልባቸው ጉዳዮች ዙርያ ከዘምዘም ባንክ ጋር የመግባቢያ ስምምነት ሰነድ ባለፈው ረቡዕ ግንቦት 9 ቀን 2015 ዓ.ም በሕብረት ባንክ ዋና መሥርያ ቤት ተፈራርሟል፡፡
በዚህ ስምምነት መሰረትም፣ ሁለቱ ባንኮች በቴክኖሎጂ እውቀት ሽግግርና ሥልጠና አብረው የሚሰሩ ሲሆን፤ ሕብረት ባንክም በዘርፉ ያለውን የካበተ እውቀትና ልምድ በማካፈል፣ ለዘምዘም ባንክ የኢንፎርሜሽን ቴክኖሎጂ ባለሙያዎች የአቅም ግንባታ ስልጠና እንደሚሰጥ ታውቋል፡፡  
የስምምነት ሰነዱ በባንኮች መካከል ሲፈረም በአይነቱ የመጀመሪያው መሆኑን የገለፁት የሕብረት ባንክ ዋና ሥራ አስፈፃሚ አቶ መላኩ ከበደ፤ ስምምነቱም በትብብርና በውድድር ውስጥ አብሮ መስራትን የሚያበረታታ፣ የውጭ ምንዛሪ ወጪን የሚያስቀርና የውስጥ ሠራተኞችን አቅም የሚገነባ ነው ብለዋል፡፡
የዘምዘም ባንክ ዋና ሥራ አስፈፃሚ ወ/ሮ መሊካ በድሪ በበኩላቸው፤ ስምምነቱ በባንኪንግ ኢንዱስትሪው ትልቅ ምዕራፍ መሆኑን ገልፀው፣ የውጭ ምንዛሪ ወጪን ለማስቀረትና የዕውቀት ሽግግርን ለማድረግ ያስችላል ብለዋል፡፡ በቀጣይም ሁለቱ ባንኮች የጋራ ተጠቃሚነትን በሚያረጋግጡ የተለያዩ ሥራዎች ላይ በቅንጅት ለመሥራትና የልምድ ልውውጥ ለማድረግ ከስምምነት ላይ መድረሳቸው ታውቋል፡፡
 ሕብረት ባንክ “ኦራክል ፍሌክስኪዩብ ኮር ባንኪንግ ሲስተም”ን በራሱ ከመተግበሩ ባሻገርም፣ በቅርቡ የሞባይል ባንኪንግ አፕሊኬሽኑንም በራሱ የኢንፎርሜሽን ቴክኖሎጂ ባለሙያዎች ማዘመኑ የሚታወቅ ነው፡፡

ኤሊት ፊንቴክስ ሶሉሽንስ ኃ/የተ/የግል ማኀበር፣  ኢ- ብድር በተሰኘ ሲስተም አማካኝነት፣ “ብድር ለገበሬውና ብድር ለወጣቱ”  የተሰኘ ኢንሽዬቲቭ፣ ባለፈው ረቡዕ  በሀርመኒ ሆቴል ይፋ አደረገ፡፡ የድርጅቱ ዋና ሥራ አስፈፃሚ አቶ አልአዛር ሰለሞን  እንደተናገሩት፤  በማኀበራዊ ክሬዲት ኢንሽየቲቭ ሥር፣ “ብድር ለገበሬ፣ ብድር ለወጣቶች” በሚል በድምሩ ሁለት ሚሊዮን ዜጎችን በኢ - ብድር ክሬዲት ማኔጅመንት ሲስተም ለመድረስ አቅዶ እየተንቀሳቀሰ ይገኛል፡፡ አንድ ደንበኛ በኢ- ብድር አማካኝነት ተመዝግቦ ለባንኮች የብድር ጥያቄ ለማቅረብ አስፈላጊ መረጃዎች ከ5 ደቂቃ ባልበለጠ ጊዜ ውስጥ እንደሚጠናቀቁ የገለፁት አቶ አልአዛር፤ ባንኮች ሥራውን በተናጠል ሲያከናውኑ የብድር አናሊስስ መሥራት ብቻውን ወራትን ይፈጅባቸው እንደነበር በማስታወስ፣ ኢ- ብድር ይህን ችግርም በአስተማማኝ መልኩ ይፈታል ብለዋል። ገበሬዎች በእጃቸው የሚገኘውን መሬት፣ ከብቶች፣ የንብ ቀፎ በዋስትና በማስያዝ እንዲበደሩ የሚያስችል ሕግ ትግበራ ላይ በገጠመው ችግር በአመዛኙ ተፈፃሚ አለመሆኑን በመጥቀስ፣ የኢ-ብድር ሲስተም ይኸንን ችግር ለመቅረፍ እንደሚያስችል ተናግረዋል።


 የብልፅግና አመራሮች የም/ቤት አባላትን “ም/ቤቱን ለቃችሁ ውጡ” እያሉ ነው


         ብፅግና ፓርቲ፤ በደቡብ ክልል ህዝብ ም/ቤት፣ የቁጫ ህዝብ ተወካዮች የሆኑ የም/ቤት አባላትን “ከም/ቤት አባልነት አሰርዣችኋለሁ” በማለትና ደብዳቤውን ለሚዲያ በማሰራጨት በቁጫ ህዝብ ዴሞክራሲያዊ ፓርቲ አመራሮችና አባላት ላይ የሰብአዊ የመብት ረገጣ እየፈጸመ ነው ሲል ከሰሰ።
ሰኔ 14 ቀን 2013 ዓ.ም በተካሄደው አገራዊና ክልላዊ ምርጫ፣ በቁጫ ምርጫ ክልል የብልፅግና ፓርቲን ጨምሮ ሰባት የፖለቲካ ፓርቲዎች ቢወዳደሩም የቁጫ ህዝብ ዲሞክራሲያዊ ፓርቲ (ቁሕዴፓ) ያቀረባቸው ዕጩዎች በአብላጫ ድምጽ ማሸነፋቸውን ያመለከተው ፓርቲው፤ ውጤቱን ከብልጽግና ፓርቲ ውጭ ያሉ ፓርቲዎች በጸጋ መቀበላቸውን ይገልፃል።
በተቃራኒው ብልፅግና ፓርቲ በምርጫ በመሸነፉ ምክንያት አኩርፎ በርካታ የምርጫ ሥነ-ምግባር ጥሰቶችን በመፈጸም መራጭ ህዝቡንና በየደረጃው ያሉ የቁህዴፓ አባላትን በማሰር፣ በመደብደብና በገንዘብ በመቅጣት በሃይል ከፓርቲው እንዲወጡ አስገድዷል ብሏል- ፓርቲው። የቁጫ ሕዝብ ዲሞክራሲያዊ ፓርቲ ከትላንት በስቲያ ሐሙስ ቦሌ በሚገኘው የፖለቲካ ፓርቲዎች የጋራ ም/ቤት ቢሮ በሰጠው ጋዜጣዊ መግለጫ፤ የቁሕዴፓ አመራርና አባላት በብልፅግና ፓርቲ እየደረሰባቸው ነው ያለውን ሰብአዊና ዲሞክራሲዊ መብት ረገጣ በዝርዝር ገልጿል።
በምርጫው መሸነፉን ተከትሎ፣ የቁጫን የህዝብን ቀልብ መሳብ ያልቻውና የህዝብን ድጋፍ ይሁንታ ያላገኘው የብልፅግና ፓርቲ፣ ከህግ አግባብ ውጭ የቁህዴፓ አመራርና የደቡብ ክልል ሕዝብ ተወካዮች ም/ቤት የቁጫ ህዝብ ተወካዮች የሆኑ ሦስት የም/ቤት አባላትን “ከምክር ቤት አባልነት አሰርዣለሁ” የሚል ደብዳቤ በተለያዩ ሚዲያዎች ማሰራጨቱን የጠቆመው ቁህዴፓ፤ ይህም ሳይበቃው በቁጫ ምርጫ ክልል በሁሉም መዋቅሮች “የቁህዴፓ ተወካዮች ከም/ቤቱ ተባርረዋል” በማለት የደስታ መርሃ ግብር በማሰናዳት ተወካዮቹን በመረጠው ህዝብና  በፓርቲው አባላትና ደጋፊዎች ዘንድ ቁጣና ግጭት እንዲፈጠር የተለያዩ ቀስቃሽ ድርጊቶችን በመፈጸም ላይ ይገኛል” ብሏል- በመግለጫው።
“የደቡብ ክልል ም/ቤት፤ አንድ አባል ከም/ቤት አባልነት ሊወጣ የሚችልበት የህግ አሰራና ሂደትን በሚጣረስ መልኩ “የቁጫ ህዝብ ተወካዮች ከክልል ም/ቤት አባልነት ተሰርዛችኋል” በማለት ያሰራጨው ደብዳቤ፣ የምርጫ ህግና ሥርዓት ዋጋ እንዲያጣ ብሎም በሃገራችን የተጀመረው ሰላማዊ የፖለቲካ ትግልና መድብለ ፓርቲ ዴሞክራሲ ስርዓት ግንባታ ወዳልተፈለገ አቅጣጫ እንዲገባ የሚገፋፉ ኢ- ህገመንግስታዊ ድርጊት ነው።” ሲል ኮንኗል። የህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት አባል የሆኑት ተባባሪ ፕ/ር ገነነ ገደቡ በቁጫ ሰላምበር የግድያ ሙከራ ሲደረግባቸው ም/ቤቱ ምንም አለማለቱ ጥሩ መልዕክት የሚያስተላልፍ አይደለም ለምክርቤቱም ክብር የሚመጥን አይደለም ሲል ፓርቲው አማርሯል።“ይህ አድራጎት በሰላማዊ ትግል መስመር ብዙ ጫናዎችን አልፎ ይወክለኛል ያላቸውን ተወካዮቹን ለውክልና ያበቃውን ህዝብ በእጅጉ መናቅና ከህገመንግስቱ ድንጋጌዎች ጋር በእጅጉ የሚቃረን እንዲሁም በአገራችን የዲሞክራሲ ስርዓት ዕድገትን ለማምጣት የምናካሂደውን ጥረት የሚያጨናግፍ ነው” ብሏል- ፓርቲው።
በሌላ በኩል በደቡብ ክልል በጋሞ ዞንና በቁጫ ሦስቱም መዋቅሮች የብልፅግና ፓርቲ ገና ሊካሄድ የታቀደውንና በብዙዎች ዘንድ ተስፋ የተጣለበትን የሃገራዊ ምክክር ሂደትን ዋጋ የሚያሳጣ የሴራ ድራማ ላይም መትጋቱን ቁህዴፓ ይገልፃል።
በዚህም መሰረተ ብልፅግና “ሚያዚያ 28 እና 29 ቀን 2015 ዓ.ም በአርባ ምንጭ በቁጫ ሰላምበር ከተሞች  “የቁጫ ህዝብ የእርቀ ሰላም ኮንፍረንስ” ማካሄዱን የጠቀሰው ቁህዴፓ፣ የቁጫ ህዝብ ህጋዊ ተወካይ  ሆን ተብሎ ባልተጋበዘበት ከተፎካካሪ የፖለቲካ ፓርቲዎች ማንም ባልተሳተፈበት፤ የምክክር ተግባራትን እንዲያከናውን ሥልጣን የተሰጠው የአገራዊ ምክክር ኮሚሽን በማያውቀው መልኩ፣ የገዛ ራሱን ካድሬዎች ሰብስቦ መላውን መራጭ ህዝብ በአስነዋሪ ሁኔታ በሚያንኳስሱ መፈክሮች የተሞላ ጉባኤ ማድጉን በመግለጫው አመልክቷል።
“ገዢው ፓርቲ ብቻውን ተሰብስቦ ራሱ አጥፊ፣ ራሱ አስታራቂ፣ ራሱ ከራሱ ጋር ታራቂ የሆነበትንና የቁጫ ህዝብንና በቁጫ የሚንቀሳቀሱ የፖለቲካ ሃይሎችን ያላማከለ “ድራማ” መሰራቱ ሳያንስ፤ ጉባኤውን “የህዝብ ሃሳብ የተንጸባረቀበት ነው” በሚል ለፌደራል መንግሥት ባለስልጣናት ሪፖርት  ማድረጉ ከባድ የማጭበርበር ተግባር ነው ሲል ወቅሷል- ፓርቲው። ከዚህ አንፃር የሚመለከታቸው የፌደራል መንግስት አካላት ተደርጓል የተባለውን የእርቀ ሰላም ሂደት ምን ይመስል እንደነበር  በገለልተኛነት እንዲያጣሩም ጥሪ አቅርቧል።
እነዚህን መሰል ኢ-ሰብአዊና ህገ-መንግሥታዊ ተግባራት በጋሞ ዞን ባሉና ተፎካካሪ ፓርቲዎች የህዝብ ይሁንታ ባገኙባቸው የቁጫና የዛይሴ ምርጫ ክልሎች በገዢው ፓርቲ ትውልድ ይቅር የማይሉት በደሎች እየተፈጸሙ ናቸው ያለው ቁጫ ህዝብ ዴሞክራሲያዊ ፓርቲ፤ በእነዚህ አካባቢዎች ገዢው ፓርቲ ሰላማዊ ትግልን ወደ ጎን የመተውን አካሄድ ትቶ፣ ለማናቸው የህዝብ ጥያቄዎች ጆሮ እንዲሰጥ እንዲሁም፣ የታችኛው የመንግስት ባለስልጣናትን ገደብ ያጣ አምባገነንነትና ሌብነት እንዲያስቆም እንጠይቃለን ብሏል። ከሁሉም በላይ ደግሞ ማንም እየተነሳ የምክር ቤት አባላትን “የምክር ቤት መታወቂያ ካርዳችሁን ተመላሽ አድርጋችሁ ም/ቤቱን ለቃችሁ ሂዱ” እያሉ ኢ-ህገመንግሥታዊ ብይን እንዳይሰጡ መንግስት የማያዳግም እርምጃ ፓርቲው፤ የብሄር ማንነትና የራስ አስተዳደር የህዝብ  ጥያቄዎችም በህገ-መንግስቱ መሰረት አፋጣኝ ምላሽ እንዲሰጣቸውና በመላ አገሪቱ እውነተኛ ፍትህን ማረጋገጥ እንዲቻል ጥሪውን አቅርቧል።

ባለሃብቱ፤ ሆቴሉን እንድሰራ ያደረገኝ የህዝቡ ፍቅር ነው ብለዋል

ከአዲስ አበባ በስተሰሜን በቅርብ ርቀት ላይ በምትገኘው ሰንዳፋ በኬ ከተማ ድንገት የበቀለ የሚመስል ባለ ግርማ ሞገስ ድንቅ ሆቴል ቆሞ ይታያል፡፡ በእርግጥ ለከተማዋ ነዋሪና አካባቢውን ለሚያውቅ ሰው ድንገት የበቀለ አይደለም፡፡ ግንባታውን ለማጠናቀቅ ከ5 ዓመት በላይ ጊዜና 450 ሚሊዮን ብር ፈጅቷል፡፡

የበኬ ከተማ ሃብትና ጌጥ እንደሆነ የተነገረለት ይኸው "ቱ አር ኤን ሰለሞን ሆቴልና ስፓ"፣ ከግንቦት 19 ቀን 2015 ዓ.ም ጀምሮ ለተከታታይ ቀናት እንደሚመረቅ ነው የተገለጸው፡፡

በቀድሞው የደርግ መንግሥት ጦር ሠራዊት ውስጥ አገራቸውን በወታደርነት ባገለገሉት መቶ አለቃ ሰለሞን አዳሙ የተገነባው ይህ ባለ  5 ኮከብ ሆቴል፣ ዛሬ ረፋድ ላይ በሚዲያ ቡድን አባላት የተጎበኘ ሲሆን ጋዜጣዊ መግለጫም ተሰጥቷል፡፡

በ1982 ዓ.ም የደርግ መውደቅን ተከትሎ፣ የድለላ ሥራ መጀመራቸውን  የሚናገሩት መቶ አለቃ ሰለሞን፤ በኋላም በ3ሺ ብር ካፒታል ወደ ንግድ ሥራ መግባታቸውን ያስታውሳሉ፡፡ ባለሃብቱ በከተማችን  የሚታወቀው የቱ አር ኤን ሰለሞን ፈርኒቸር  ባለቤት ሲሆኑ፤የሆቴሉ ህንጻ የእንጨት ሥራዎች በሙሉ የተከናወኑት በዚሁ ድርጅታቸው ነው ተብሏል፡፡

በሰንዳፋ በኬ ከተማ በ2ሺ ካ.ሜ ቦታ ላይ በግርማ ሞገስ የተንጣለለው ሆቴሉ፤ደረጃቸውን የጠበቁና ዘመናዊ ቴክኖሎጂ የተገጠመላቸው 40 የመኝታ ክፍሎች አሉት፡፡ ከሬስቶራንት ባርና ካፌ በተጨማሪም የጃኩዚና ስፓ አገልግሎቶችን ይሰጣል፡፡

በተለይ የአካባቢው ቀዝቃዛ አየርና ያማረ ተፈጥሯዊ ዕይታ  ሆቴሉን ተመራጭና ተወዳጅ እንደሚያደርገውም ተነግሯል፡፡

ሆቴሉ ያረፈበትን ቦታ በ2009 ዓ.ም መውሰዳቸውን የተናገሩት መቶ አለቃ ሰለሞን፤ የሊዝ ክፍያውን የፈጸሙት የቀድሞው ጠ/ሚኒስትር ኃይለማርያም ደሳለኝ ሥልጣን  መልቀቃቸውን ያስታወቁ ዕለት መሆኑን ለጋዜጠኞች ገልጸዋል፡፡

በአማራ ክልል ጎጃም ውስጥ የተወለዱት ባለሃብቱ፣ የጸጥታና ደህንነቱ ሁኔታ እጅግ አስጊ በነበረበት ወቅት መዋዕለንዋያቸውን እንዴት በኦሮሚያ ክልል በምትገኘው የሰንዳፋዋ ቤኪ ከተማ ለማፍሰስ እንደደፈሩ ተጠይቀው ነበር፡፡ መቶ አለቃ ሰለሞን ሲመልሱም፤ "የእኛ ካሜራ የአካባቢው ህዝብ ነው፤ኮሽ ባለ ቁጥር ህዝቡ ነው ሆቴሉን ወጥቶ ከአደጋ የሚጠብቀው፡፡ የአካባቢው ህዝብ ፍቅር ነው ይህን ሆቴል ያሰራኝ፡፡" ብለዋል፡፡

ባለሃብቱ አክለውም፤ "ረብሻና ግርግር በነበረበት ወቅት ወደ አዲስ አበባ ስመለስ የአካባቢው ነጋዴዎች  በመኪና አጅበው ለገጣፎ ድረስ ይሸኙኝ ነበር፡፡" ሲሉ የህዝቡን ፍቅር ገልጸዋል፡፡

ይህንን እውነታ ለጋዜጠኞች መግለጫና ማብራሪያ የሰጡት  የከተማዋ ከንቲባ አቶ አለማየሁ ተንኮሉም አረጋግጠውታል፡፡  በኬ የሁሉም ብሔር ተወላጆች በሰላምና በፍቅር የሚኖሩባት ከተማ ናት የሚሉት ከንቲባው፤ ህብረተሰቡ መቶ አለቃ ሰለሞን የገነቡትን ሆቴል እንደራሱ ንብረት እንደሚያየውና እንደሚሳሳለት ተናግረዋል፡፡

በአካባቢው ያሉትን ሃብቶች ለጋዜጠኞች በዝርዝር የጠቀሱት ከንቲባ አለማየሁ፤አሁን ደግሞ ሌላ ሃብት ጨምረናል ብለዋል - ባለ 5 ኮከቡን አስደማሚ  ሆቴል ማለታቸው ነው፡፡ ሃቀኛ አልሚዎችን ብዙ ርቀት ተጉዘው እንደሚያስተናግዱ በመግለጽም፤ ኢትዮጵያውያን ባለሃብቶች ወደ ከተማዋ መጥተው ኢንቨስት እንዲያደርጉ ጥሪ አቅርበዋል፡፡



•   አንድ ባጃጅና 2 ሞተርሳይክሎችንም ለአሸናፊዎች ሸልሟል

ሳፋሪኮም ከወር በፊት ከ1ሚሊዮን በላይ ደንበኞችን ተሸላሚ የሚያደርግ "ተረክ በጉርሻ" የተሰኘ አገር አቀፍ የሽልማት መርሃ ግብር በይፋ ማስጀመሩ የሚታወስ ሲሆን፤በዛሬው ዕለት የመጀመሪያዎቹን የከፍተኛ ሽልማቶች አሸናፊዎች ይፋ በማድረግ፣ የመኪና የባጃጅና የሞተር ሳይክሎች ሽልማቶችን አበርክቷል፡፡

 የዕጣው አሸናፊ ተሸላሚዎች  የአዲስ አበባውን  የመኪና አሸናፊ፣ የአዳማውን የባጃጅ አሸናፊ እንዲሁም የአፋርና የድሬዳዋውን የሞተርሳይክል  አሸናፊዎች  ጨምሮ ከመላው አገሪቱ በርካታ ስልኮችና ታብሌቶችን ያሸነፉ ደንበኞች እንደሚገኙበት ሳፋሪኮም አስታውቋል፡፡

ኩባንያው በዛሬው ዕለት ረፋድ ላይ አውቶብስ ተራ፣ ማማድ ህንጻ ላይ በሚገኘው  የሳፋሪኮም አከፋፋይ ሱቅ ባዘጋጀው አሸናፊዎችን ይፋ የማድረግ  ሥነሥርዓት ላይ ነው፣ ለባለዕድለኞች  ሽልማታቸውን ያበረከተው፡፡

ሳፋሪኮም ባዘጋጀው በዚህ "ተረክ በጉርሻ" የተሰኘ አገር አቀፍ የሽልማት መርሃግብር፣ የመጀመሪያውን የመኪና ሽልማት ያሸነፈው የአዲስ አበባው፣ የጉርድ ሾላ ነዋሪ፣ ሙባረክ ሱሩር መሆኑ ታውቋል፡፡

ሙባረክ እንዴት ሽልማቱን እንዳሸነፈ ተጠይቆ በሰጠው ምላሽ፤"የሳፋሪኮም መስመርን ለጥቂት ጊዜ ስጠቀምበት ቆየሁና እኔ ሌሎች ዘመዶችን ለመጠየቅ ወደ ገጠር ስሄድ እዚህ ላለ ዘመዴ ሰጠኹት፡፡ በ0700 700 700 ሲደወል ዘመዴ ነበር የመለሰው፤ከዚያም ሽልማቱን ማሸነፌን አስታወቀኝ፡፡ መኪናውን ማሸነፌን ስሰማ በጣም ነው ደስ ያለኝ፡፡ የዕጣ ሽልማት መጀመሩን አውቅ ነበር፤ነገር ግን መኪና አሸንፋለሁ የሚል ሃሳብ ወደ አዕምሮዬ መጥቶ አያውቅም፡፡ እጅግ አስደሳች ዕድል ነው፤ድንገተኛ! ሁሉም ሰው እንደኔ የማሸነፍ ዕድል እንዲያገኝ የሳፋሪኮም መስመርን እንዲጠቀም እመክራለሁ፡፡" ብሏል፡፡

የአዳማው ናኦሊ መሃመድ፣ ሁለተኛውን የባጃጅ ሽልማት ያሸነፈ ሲሆን፤ ሁለት ሞተርሳይክሎችን ደግሞ የድሬዳዋው አሸናፊ ታደሰ አሰፋና የአፋር ክልሉ ሙክታር ሞሃመድ አሸንፈዋል፡፡

ሁለተኛውን የደንበኞች የአሸናፊዎች ቡድን ለመሸለም በመብቃታቸው በስሜት መጥለቅለቃቸውን የገለጹት የሳፋሪኮም ኢትዮጵያ ሪጂናል የሽያጭ ማናጀር አቶ ቢኒያም ዮሐንስ፤ አገር አቀፉ የዕጣ ሽልማት መርሃ ግብር ተጨማሪ በርካታ ደንበኞቹን መሸለሙን እንደሚቀጥል አስታውቀዋል፡፡

የዛሬ ወር ገደማ የዕጣ ሽልማት መርሃግብሩ ይፋ ከተደረገ ወዲህ፣ ተጨማሪ 400ሺ ደንበኞች  ዕለታዊ የአየር ሰዓት ሽልማቶች ማሸነፋቸውንም ኩባንያው በመግለጫው አስታውቋል፡፡

ሳፋሪኮም በመጪዎቹ ሰባት ሳምንታት ለበርካታ ተጨማሪ ደንበኞቹ፤ ሁለት መኪኖችን፣ 5 ባጃጆችን፣በርካታ ስልኮችንና ታብሌቶችን እንዲሁም የአየር ሰዓቶችን እንደሚሸልምም አስታውቋል፡፡

የሽያጭ ሃላፊው አቶ ቢኒያም ዮሐንስ ባስተላለፉት መልዕክትም፤ "እንደ ሳፋሪኮም ደንበኛ አገልግሎታችንን ስትጠቀሙ በየዕለቱ ተጨማሪ እሴት ታገኛላችሁ፤ማንኛውም ሰው የ07 ኔትዎርኩን በመቀላቀልና የሳፋሪኮም መስመርን በየዕለቱ በመጠቀም የዕጣ ሽልማቶች የማሸነፍ  ዕድሉን ማሳደግ ይችላል" ብለዋል፡፡

የኮንስትራክሽን ፤የቤት ሻጮችና ገዢዎች፤ አንዲሁም ገንቢዎችና የተለያዩ ተቋማትን ለማገናኘትና ለማስተሳስር እድል የሚሰጠው አርኪ የሪል እስቴት ኤክስፖ በዛሬው እለት ተከፍቷል።

ከዛሬ ግንቦት 5 እስከ 7 ቀን 2015 ዓ.ም ለሦስት ቀናት በሚዘልቀው  ኤክስፖ፤ በርካታ የቤት አልሚዎች እየገነቡት ያሉት ቤቶች የሚገኙበትን  ደረጃ ፣ የቤቶቹን ዋጋ ፣ ሊገነቡት ስላቀዱት ቤት ፣ ስለሚፈልጉት  እቃ እና አገልግሎት ከኤክስፖ ተሳታፊዎችና ጎብኚዎች ጋር መረጃና ልምድ ይለዋወጣሉ ተብሏል፡፡

አርኪ ኤቨንት ኦርጋናይዘር  ባዘጋጀው በዚህ  ኤክስፖ  ላይ ለሽያጭ ባለሙያዎች ነፃ ስልጠና እንደሚሰጥና  የፓናል ውይይቶች እንደሚካሄዱ ታውቋል፡፡

   ንጉሳዊው ሥርዓት ከዙፋኑ ላይ አልወረደም፡፡ የኢትዮጵያ ፖለቲካም ለትጥቅ ካልሆነ ለፓርቲ ትግል አልታደለም፡፡ በ1953 የመፈንቀለ መንግስት ሙከራ የተደረገባቸው ቀዳሚው ኃይለስላሴ ያንን ክፉ ቀን አስታውሰው አንፃራዊ ነፃነትን ይሰጣሉ ተብሎ ቢጠበቅም የሆነው ግን ተቃራኒው ነው፡፡ ንጉሳዊ አስተዳደሩ ፍፁም አምባገነናዊ እየሆነ ሔደ፡፡ ሜጫና ቱለማ የመረዳጃ ማኀበርን የመሰረቱት የኦሮሞ መብት ተቆርቋሪዎችም መጨረሻቸው የሚያምር አልነበረም፡፡ ብልጭ ያለው ትግል ለአፍታ አሸለበ፡፡
ይሁንና በእዚያው አላንቀላፋም፡፡ በ1960 (እ.ኤ.አ 1967) የብሔሮች ጭቆና ያገባናል ያሉ ወጣቶች የህቡዕ አደረጃጀትን ፈጥረው የኢትዮጵያ ብሔራዊ ነፃ አውጭ ግንባርን መሰረቱ፡፡ በ”ሶርያ”ና በየመን ወታደራዊ ስልጠናን ወስደው ለማይቀረው ትግል የተዘጋጁት የምስጢራዊ ቡድኑ አባላት አዲስ አበባ ውስጥ መዋቅራቸውን ለመዘርጋትም እንቅስቃሴ ጀመሩ፡፡ “ሶርያ” የከረሙት የድሬዳዋ ተወላጆቹ መኸዲ መሐመድ እና ሙሣ ቡሽትም ተልእኳቸውን መሬት ለማውረድ አብሯቸው የሚኖረውን ሰው የሕቡእ አደረጃጀቱ አባል አደረጉ፡፡
አሊ መሀመድ ሙሣ ከሁለቱ ወጣቶች መረጃዎችን እየተቀበለ ለሌሎች ማድረስና ማደራጀት ላይ መሳተፉን ቀጠለ፡፡ በዚህ ሂደት ውስጥ እያለም ነበር ድብቋ አሜሪካ ግቢ አካባቢ የሚኖርባት ቤት ድንገት የተንኳኳችው፡፡ በሩን ከፈተው፡፡ አንድ ሰው መኸዲ መሐመድን እንደሚፈልግ ነገረው፡፡ አብሮት የሚኖረውን ሰው ለመጥራት አላንገራገረም፡፡
መኸዲን ከፊቱ ያለውን ሰው አቤት አለው፡፡ 200 ብር ተልኮልህ እርሱን ለመስጠት ነበር ብሎ መልዕክተኛው እጁን ወደ ኋላ ኪሱ ላከ፡፡ የመዘዘው ግን የብር ኖቶችን አልነበረም፡፡ ሽጉጥ አውጥቶ የፖለቲካ ተሳትፏቸውን መንግስት እንደሚያውቅ ተናግሮ፣ ወደ ፖሊስ ጣቢያ እንዲሔዱ አዘዛቸው፡፡ አሊ መሀመድ ሙሳ በቀዳማዊ ኃይለ ሥላሴ የደህንነት ሰዎች እጅ መውደቁን ሲረዳ ማታ የምለብሰው ነገር ብቻ ልያዝ ብሎ ወደ ቤቱ ተመልሶ ገባ፡፡ ሳያመነታ በመስኮት አንድ ፎቅ ወደ ታች ዘሎ አመለጠ፡፡
አሊ መሃመድ ሙሳ የመድረክ ስሙን የአዘቦት መጠሪያው ያደረገ ድምፃዊ ነው፡፡ ግን ይኼም ታሪክ ከፖለቲካ አላመለጠም፡፡ በ14 ዓመት እድሜው የ”አፍራን ቀሎ” የሙዚቃ ቡድን አካል ከሆነው “ሂሪያ ጃለላ” የታዳጊዎች ስብስብ ጋር የመጀመሪያ ዜማው “ቢራ ዳ በርሄን” ሲጫወት “ፀሀይም አበራች አበቦቹም ፈኩ፤ አቤቱ አምላኬ እኔ ምን በደልኩ” ሲል አንጎራጉሯል፡፡ ታዳሚው በትንሹ ልጅ አጨዋወት ተማርኮ የላቀ አድናቆቱን ለገሰው፡፡ የመጀመሪያ ስራውም የአባቱን ስም አስረሳች፡፡ አሊ መሀመድ መባሉ ተረስቶ አሊ ቢራ በሚለው ናኘ፡፡ አሊ ትውልዱ ድሬዳዋ ነው፡፡ የአባቱ ስም መሀመድ ሙሳ ሲሆን የእናቱ ስም ደግሞ ፋጡማ አሊ ይባላል፡፡ አሊ፤ አሊ የተባለው አያቱን (የእናቱን አባት) ለማስታወስ ነው፡፡
ይሁንና የወይዘሮ ፋጡማን አባት ስም መጠሪያው ያደረገው አሊ ከእናቱ ስምን እንጅ ፍቅርን አልወረሰም፡፡ ገና በሕፃንነት እድሜው ወላጆቹ ፍች በመፈፀማቸው አባቱ ጋር ቀረ፡፡ የመሀመድ ሙሳ ገቢ አነስተኛ መሆን ደግሞ  ከአባቱም ነጠለው፡፡ አቶ መሀመድ ለአጎታቸው የትዳር አጋር ወይዘቶ ሜይሮ አሊ አደራ ሰጡ፡፡ ሜይሮ ከአቶ መሀመድ ቢሻሉ እንጂ የእሳቸውም የገቢ ምንጭ እንጀራ መሸጥ ነበር፡፡ እናም ታዳጊው አሊ እንጀራ የመሸጥ ኃላፊነት በለጋ እድሜው ወደቀበት፡፡ የአሊ ለስላሳ የህይወት ዜማ ጅማሮው ያኔ ነው፡፡”አለ ትኩስ እንጀራ አለ” እያለ የሚሸጥበት መንገድ ለዛ ያለው ነበረ፡፡ ከሰፊዋ ዓለም ያገኛት ትንሿ ቀዳሚ የሙዚቃ መድረክ እሷ ሳትሆን አትቀርም፡፡ ዜማና ማንጎራጎር ለመደባት፡፡
አቶ መሀመድ ለራሳቸው የሚሆን ቁራሽ ቢያጡም ለልጃቸው ግን የቻሉትን ሁሉ ለማድረግ መፍጨርጨራቸው አልቀረም፡፡ በመሆኑም የእስልምና ትምህርትን እንዲከታተል አስመዘገቡት፡፡ ቁርዓን ሊቀራ ከዕኩዮቹ ጋር ዋለ፡፡ የአቶ መሀመድ ዓረብኛ መቻል ደግሞ ቋንቋውን አቀለለለት፡፡ ከአምስት ዓመት በኋላም ተመረቀ፡፡ አሊን በሃይማኖታዊ አገልግሎት የጠበቁት አልታጡም፡፡ ልጅነቱን እየተሰናበተ የነበረው ታዳጊ ግን ለራሱ መሀንዲስ ሆኖ አቅጣጫውን ቀየሰ፡፡
ጓደኞቹ ወደ ነገሩት “አፍራን ቀሎ” የሙዚቃ ቡድን ሄዶም ተመዘገበ፡፡ አባልነቱ አንጋፋዎቹ የሙዚቃ ቡድኑ አባላት በደረሱለት ሶስት ዜማዎች ታጅቦ ከህዝብ ፊት አቆመው፡፡ “ቢራ ዳ በርሔ” በድሬዎች መንደር ተወዳጅ ሆነች፡፡ አላቆመምም፡፡ የተለያዩ የዓረብኛ፣ ሱዳንኛ እንግሊዝኛ ዜማዎችን እየተዋሰ የሚሰራቸው የኦሮምኛ ሙዚቃዎች ከዕድሜው በላይ የእውቅና ከፍታ ላይ ሰቀሉት፡፡ ይሁንና የድሬዳዋና “አፍራን ቀሎ”ን ፍቅር ፖለቲካ መረዘው፡፡ እነዛ አሊን የወደዱ የሙዚቃ አፍቃሪያንም ትንሹን ልጅ ከዓይናቸው አጡት፡፡ ምክንያቱ ደግሞ ስደትን መርጦ ወደ ጂቡቲ ጉዞ መጀመሩ ነበር፡፡
ይሁንና ጂቡቲ የነበሩ ወታደሮች ሕገ-ወጥ ነው ብለው ወደ እስር ቤት ወረወሩት፡፡
 የአምስት ወራት እንግልቱን ሲጨርስ አማራጭ አልነበረውም፤ ወደ ኢትዮጵያ ተመለሰ፡፡
የትውልድ መንደሩ ግን የጠፋባትን ልጅ በደስታ አልተቀበለችውም፡፡ የንጉሱ የደህንነት ሰዎች አሊና ጓደኞቹን በፖለቲካ ክስ ወደ ማረሚያ ላኳቸው፡፡ በትንሹ ልብ ውስጥ የበቀለው የፖለቲካ ተሳትፎ ነፍስ የዘራው አሳሪዎቹ ወደ ጠቅላይ ግዛቱ መቀመጫ ሐረር በ1957 ካዛወሩት በኋላ ነበር፡፡ በነፍስ ማጥፋት ወንጀል ተጠርጥሮ የታሰረ አንድ ወጣት በፖሊሶች ይህ ቀረሽ የማይባል ግፍ ሲፈጸምበት ያስተውላል፡፡
በአሊ ገለጻ ተጠርጣሪው ወንጀሉን አለመፈጸሙ እሙን ቢሆንም፣ ፖሊሶች ግን የጭካኔ በትራቸውን ለአፍታ ሊያስቀምጡ አልወደዱም፡፡
በመጨረሻም ስቃዩ የከበደው ሰው ያላደረገውን ወንጀል አመነላቸው፡፡ አላመነቱም፡፡ በፍርድ ቤት አስወስነው በስቅላት ገደሉት፡፡ አሊ ከትንሿ የእሥር ክፍሉ ሆኖ ያን ሰው ሲያጣጥር አይቶታል፡፡ ኋላም ላይመለስ ሲያሸልብ እንደዛው፡፡ አሊ ቢራ በልጆቿ ላይ የምትጨክነው ኢትዮጵያ ትቅርብኝ ያልኩት ያኔ ነበር ይላል፡፡ የድሬዳዋው መልከ መልካም ወደ አዲስ አበባ ያቀናው ከዚህ ሁሉ ጊዜ በኋላ በሰኔ ወር 1958 ነው፡፡
ብዙ አልቆየም፡፡ በአንድ አጋጣሚ ሲያንጎራጉር የተመለከቱት የክብር ዘበኛው ኮለኔል ጣሒር ኤልተሬ ወደ ክብር ዘበኛ ሙዚቃ ክፍል እንዲቀላቀል እድሉን አመቻቹለት፡፡ በ1959 አሊ መሀመድ ሙሳ በአገሪቱ ትልቅ የሚባለው የሙዚቃ ክፍል አባል ሆነ፡፡ ስራዎቹ አድናቆት ማግኘታቸው የትናንት አምሮቱን አልረታውም፡፡ በዚህ ምክንያትም በኦሮሞ የትግል ታሪክ ውስጥ ከግንባር ቀደሞቹ ተርታ በሚመደበው የሜጫና ቱለማ መረዳጃ ማህበር ውስጥ በሙዚቃው ድጋፍ ማድረግ ጀመረ፡፡ ለድሬዳዋው ፈናን ወግ አጥባቂው ክቡር ዘበኛ የሚመቸው አልነበረም፡፡ የሚያገኘው ገቢ ማነስ ተጨምሮበት ሙዚቃን አቁሞ አዋሽ ሌላ ስራ ጀመረ። ሙዚቃን ከአንገት በላይ ቢያኮርፋትም ልቡ ግን እሷው ጋር ነበር፡፡
“አዋሽ ነማ ሾኪሶ” የተሰኘ ስራውን ከህዝቡ ትውፊት ተውሶ ውብ አድርጎ የተጫወተው ከዛ መልስ ነው፡፡ ነፃነትን ናፋቂው አሊ፤ ከዚህ በኋላ ፊቱን ያዞረው ወደ ምሽት ክበቦች ነበር፡፡ በአብዮቱ ዋዜማ ሰሞን ጠመንጃ ያዥ አካባቢ በሚገኘው “ዋዜማ ክለብ” ሥራውን አሀዱ አለ፡፡ የጭቆና ምንጭ ነው ባለው ስርዓት ላይም በድፍረት ማዜሙን ቀጠለ፡፡ አሊ የናፈቀው አብዮት ዘገየ አንጂ አልቀረም፡፡ የቀዳማዊ ኃይለ ስላሴ ዙፋን ተገርስሶ ወታደራዊው የደርግ ሥርዓት አራት ኪሉ ደረሰ፡፡ ንጉሳዊውን መንግስት አምርሮ የሚጠላው የድሬው ፈናንም፣ ባላባቱን የሚነቅፍ “አባ ለፋ” የሚል ሙዚቃውን ይዞ ብቅ አለ፡፡
አሊ ለውጥን ቢናፍቅም በመጣው ለውጥ ለመሰላቸት ግን አፍታ አልወሰደበትም፡፡ በመሆኑም በተለያየ መንገድ ለኦሮሞ ማንነት ሲታገሉ የነበሩና ዘግየት ብለው ኦነግን ከመሰረቱ የፖለቲካ ሃይሎች ጋር በቅርበት መስራት መረጠ፡፡ እነዚህ ወገኖች ድሬዳዋ ያሉ የሙዚቃ ሰዎችን አምጥተህ ስልጠና ስጥልን ባሉት መሰረትም ስልጠና ሰጠ፡፡
 አሊ መሀመድ ሙሳ ወዲህ የኦሮሞን ማንነትና ባህል ለማስተዋወቅ እየታገለ ወዲያ በምሽት ቤቶች ስሙ መናኘት ጀመረ፡፡“ዛምቤዚ ክበብ” የተጀመረው ተወዳጅነት፣ ሜክሲኮ አቅራቢያ ባለው “ዲያፍሪክ” ሆቴል ገነነ፡፡ ማሕሙድ አህመድን የመሰሉ ተወዳጅ ድምፃዊ የያዘው በራስ ሆቴል የነበረው አይቤክስ ባንድም ከአሊ ቢራ ጋር መጣመርን መረጠ፡፡ ይህ አብሮነትም “አማሌሌ” የተሰኘ አልበሙን አዋለደ፡፡ አሊ በ1970ዎቹ አጋማሽ የእውቅና ማማ ላይ ቢደርስም የስዊድን ኤምባሲ ሰራተኛ ከነበረችው ባለቤቱ ብርጊታ አስትሮም ጋር ኑሮውን ሊያደላድል ወደ አሜሪካ መጓዙ ግን አልቀረም፡፡
ይህም ቢሆን ከሙዚቃው ሰማይ እንጂ ከኦሮሞ የትግል ጥያቄ አላራቀውም፡፡ ሳዑዲ ዓረቢያ ውስጥ “የኦሮሞ ነፃነት ግንባር” እና “የኦሮሞ እስላማዊ ነፃነት ግንባር” ያላቸውን ልዩነት በውይይት እንዲፈቱና በአንድነት እንዲታገሉ ያልተሳካ ሙከራ አድርጓል፡፡ አሊ በፖለቲካ ቡድኖች ገቢ ማሰባሰቢያ ዝግጅቶች ላይ ከፍ ያለ አስተዋጽኦ ቢኖረውም፣ ይፋዊ የፖለቲካ ፓርቲ አባልነት ግን ኖሮኝ አያውቅም ይላል፡፡ ይልቁኑስ በውጪ ዓለምም ቢሆን በያዝ ለቀቅ ሙዚቃውን ገፋበት፡፡ እንዲህ ያለው ሕዝባዊ ቅቡልነትን የያዘ ፖለቲካዊ ተሳትፎ ደግሞ በኢህአዴግ መራሹ መንግስት ላይ ጫና መፍጠሩ አልቀረም፡፡
በመሆኑም አሊን ወደ አገሩ መመለስ ትልቅ የፖለቲካ ፕሮጀክት ሆነ፡፡ የወቅቱ የኦሮሚያ ክልላዊ መንግስት ፕሬዚዳንት አቶ ጁነዲን ሳዶ የመሩት ተልዕኮ ከመግባባት ተደርሶበትም የሁለት አስርታት ስደተኛው ወደ አገሩ ተመለሰ፡፡ የአሊ መሀመድ ሙሳ ወደ አገር ቤት መመለስ በበርካታ ደጋፊዎቹ ነቀፌታን ቢያስከትልም፣ እርሱ ግን የመመለሱ አንዱ ምክንያት “በ1997 በነበረው የምርጫ ቅስቀሳ የአንድነት ኃይል የሚባሉት “ጨፍላቂ” አስተሳሰብን የያዙ ወገኖች በፖለቲካው ሜዳ ጎልቶ መታየት የፈጠረው ስጋት ነበር” ይላል፡፡
የድሬዳዋው ፈናን ወደ አገሩ ከተመለሰ በኋላ ከጊዜው የትዳር አጋሩ ሊሊ ማርክስ ጋር በመሆን የ”ቢራ ፋውንዴሽን”ን በመመስረት በትምህርት ቤቶች አነስተኛ ገቢ ያላቸው ወላጆች ልጆችን ለመርዳት ሰፊ እንቅስቃሴ አድርጓል፡፡ አሊ በረጅሙ የሙዚቃ ዘመኑ እልፍ ጊዜ ሞትን ፊት ለፊት ገጥሟል፡፡
አስቀድሞ በጉበት ካንሰር ተይዞ በተደረገለት ቀዶ ጥገና በተአምር ከሞት አምልጧል፡፡ በሌላ ወቅትም የጭንቅላት ዕጢ ቀዶ ጥገና ተደርጎለት ዳግም ሞትን ረቷል፡፡ አሊ መሀመድ ሙሳ ለሶስተኛ ጊዜ የወገብ ቀዶ ጥገና ሲደረግለትም የከፋ የጤና ችግር ገጥሞት ነበር፡፡ ይሁንና ሞትን አሳፍሮ በበርካታ መድረኮች ላይ እየተገኘ ለህዝቡ የደስታ ርችት፤ ላመነበትም የትግል ቃፊር ሆኖ ዘለቀ፡፡
ለአሊ ቢራ ሙዚቃ ምሽጉ ናት፡፡ ነፃነትና እኩልነትን አሻግሮ የሚመለከትባት፡፡ በሙዚቃዎቹ ውስጥ ሁሌም የማናጣት የድብቅ ወዳጁም ለዚህ ምስክር ናት፡፡
አንዴ በውብ ሴት፣ ሌላ ጊዜ በጨረቃ፣ ሲያሻው በፀሀይ የሚመስላት፡፡ “ሲን በርባዳ ሆጉ”፣”ኦሮሞ ቦሩ”፣”ያ ሁንዴ አያና” እና “ገመቹ” ውስጥ ያች ውብ ተዚሞላታል፡፡ በአሊ ቢራ ሙዚቃዎች ላይ ትንታኔ የፃፈው ዘመድኩን ምስጋናው፤ በአሊ ሙዚቃዎች ውስጥ ያለችው ሴት ቅኔ ፍች “ኦነግ” ነው ይላል፡፡ የመሀመድ ሙሳ ልጅ በይፋ አይንገረን እንጂ ስለ ኦነግ አብዝቶ በስስት ተጫውቷል፡ በአደባባይ ስለ ኦሮሞ ህዝብ ያለውን አስተሳሰብ ተናግሯል፡፡
“አኒስ ቢያን ቀባ” (የአገር ፍቅር) እና “አዴ ኦሮሚያ” ( እምዬ ኦሮሚያ) ብሎ ኦሮሞን አምሳለ አገር አድርጎ አዚሟል፡፡
ዕውቁ የታሪክ ምሁር ፕሮፌሰር መሀመድ ሀሰን፤ አሊን ድል አድራጊ የነፃነት አርበኛ ያደርጉታል፡፡
 ምክንያታቸውም ከአምሳ አመት በፊት ኦሮምኛን በማዜሙ ለእስርና ስደት የተዳረገው አሊ፤ ከ50 ዓመት በኋላ በአገሪቱ መሪዎች ፊት የሚሸለም ስመ ገናና ወደ ከመሆን መሸጋገሩ ነው፡፡ ገለፃቸው የሙዚቃና ፖለቲካን ድንበር ያፈርሳል፡፡ አሊንም እንደ ሙዚቀኛ ብቻ እንዳንመለከተው ያስገድዳል፡፡
(ከይነገር ጌታቸው (ማዕረግ) “ጠመንጃና ሙዚቃ” መጽሐፍ የተወሰደ)


 የዓለም ምግብ ፕሮግራም ሃላፊ፤ ሩሲያ ከዩክሬን የእህል ኤክስፖርት ስምምነት ከወጣች ዓለምን መመገብ ፈታኝ እንደሚሆን አስጠነቀቁ፡፡
ሲንዲ ማክኬይን ሰሞኑን ለቢቢሲ እንደተናገሩት፣ የፊታችን ሜይ 18 ቀን 2023 ዓ.ም የጊዜ ገደቡ እንደሚያበቃ የሚጠበቀው ስምምነት መታደስ ይኖርበታል፡፡
የእህል ኤክስፖርት ስምምነቱ ዩክሬን፣ ጦርነቱ እየተካሄደም ቢሆን፣ ብዙ ሚሊዮን ቶን ምግብ እንድታጓጉዝ አስችሏታል ተብሏል፡፡ ስምምነቱን ያሸማገሉት የተባበሩት መንግስታት ድርጅትና ቱርክ ነበሩ-ባለፈው ሃምሌ ወር፡፡ዩክሬን የበቆሎ፣ ስንዴና ገብስ ትልቋ ዓለማቀፍ ላኪ አገር ስትሆን፤ባለፈው ዓመት በዓለም ምግብ ፕሮግራም ከተከናወነው የስንዴ ግዢ ከግማሽ በላይ የሚሆነው የተገኘው ከዩክሬን እንደነበር ታውቋል፡፡  “ስምምነቱን ማደስ አለባቸው፡፡ ካላደሱ በስተቀር እንኳን ዓለምን ቀርቶ ክልሉንም መመገብ አንችልም፡፡” ብለዋል፤ የዓለም ምግብ ፕሮግራም ሃላፊዋ፡፡ “እንደምታውቁት ዩክሬን የአውሮፓ የዳቦ ቅርጫት ነበረች፣ አሁን ግን ያ እየሆነ አይደለም፤ እናም እህሉን ከዚያ ማውጣት አለብን፤ ምክንያቱም ሌሎች አገራትን እየጎዳ ነው” ሲሉ አስረድተዋል፤ ሃላፊዋ፡፡
ስምምነቱ በአንድ ጊዜ የሚራዘመው ለ120 ቀናት ነው፤ ነገር ግን ሩሲያ በእህልና ማዳበሪያ ኤክስፖርቷ ላይ በገጠማት መሰናክል ሳቢያ፣ ሜይ 18 ከስምምነቱ እንደምትወጣ በመግለፅ፣ በዓለም ላይ  ሥጋት ጋርጣለች ተብሏል፡፡
ቢቢሲ እንደዘገበው፤ የሩሲያ፣ ዩክሬን፣ቱርክና የተባበሩት መንግሥታት ከፍተኛ ሃላፊዎች ስምምነቱን በማራዘም ሃሳብ ላይ ለመወያየት ባለፈው ሃሙስ በኢስታንቡል ተሰብስበው ነበር፡፡ ቁርጥ ያለ ውሳኔ ላይ ግን አልደረሱም፡፡
“ጉዳዩ በእጅጉ ያስጨንቀኛል፡፡ የተቀረውንም ወገን ሁሉ ሊያስጨንቀው ይገባል፡” ብለዋል፤ ሃላፊዋ፡፡
“ሁሉም የዓለም መሪ” ስምምነቱ እንዲታደስና ግጭቱ እንዲቆም ሁኔታዎችን በማመቻቸት ያግዝ ዘንድ ጥሪ አቅርበዋል - የዓለም ምግብ ፕሮግራም ሃላፊዋ ሲንዲ ማክኬይን፡:



Page 5 of 648