Administrator

Administrator

    ሚዩዚክ ሜይዴይ ኢትዮጵያ፣ ከኢትዮጵስ ኮሌጅ ጋር በመተባበር ነገ ከቀኑ 8፡00 ሰዓት ጀምሮ “ሠረገላ ታቦር” በተሰኘው መፅሃፍ ላይ ውይይት ያካሂዳል፡፡ በብሔራዊ ቤተ መፃህፍት እና ቤተ መዛግብት ኤጀንሲ የስብሰባ አዳራሽ በሚካሄደው ውይይት ላይ የመፅሐፉ ደራሲ መሪ ራስ አማን በላይ እና በአ.አ.ዩ የታሪክ ተመራማሪና መምህር የሆኑት አቶ አበባው አያሌው፤ለውይይት የሚሆን የመነሻ ሃሳብ ያቀርባሉ ተብሏል፡፡ ማንኛውም የሥነጽሁፍ አፍቃሪ በውይይቱ ላይ መሳተፍ እንደሚችል አዘጋጁ አስታውቋል፡፡

• በመላው ዓለም እየዞሩ በመስራት ከ5 ሚ. ብር በላይ አጠራቅመው ነበር
• እሳቸውና ባለቤታቸው በመታመማቸው ገንዘቡ በህክምና አለቀ
• አሁን ገቢያቸው ከቤት ኪራይና ከጡረታ 1500 ብር ገደማ ነው
• “ህዝቡ ሲፈልግ ያሳክመኝ፤ ያለበለዚያ ስሞት ይቅበረኝ”

    ጌታቸው መኩሪያ በሳክስፎን ተጫዋችነቱ አንቱ የተባለ አንጋፋ ባለሙያ ነው፡፡ በማዘጋጃ ቤት፣ በብሄራዊ ቴአትርና በፖሊስ ሰራዊት የሙዚቃ ክፍል ከሙዚቃ ተጫዋችነት እስከ ዋና መምህርነት አገልግሏል፡፡በ1986 ዓ.ም ጡረታ ከወጣ በኋላ በሸራተን አዲስ ሆቴል ለስምንት አመታት የሰራው አንጋፋው ሙዚቀኛ፤ ከመቶ በላይ አገራትን በሥራ አጋጣሚ ዞሯል፡፡ አልቶ ክላርኔት እና ሳክስፎን አሳምሮ የሚጫወተው አርቲስቱ፤ ከሦስት አመታት ወዲህ በህመም ምክንያት ከሚወደው ስራው ርቆ የበርካታ ሆስፒታሎችን ደጃፍ ለመርገጥ ተገድዷል፡፡ የአዲስ አድማስ ጋዜጠኛ ናፍቆት ዮሴፍ ከ81 ዓመቱ የእድሜ ባለፀጋ ከጌታቸው መኩሪያ ጋር በጤናው፣ በሙያውና በአጠቃላይ ህይወቱ ዙሪያ ሰፊ ቃለምልልስ አድርጋለች፡፡

     የጤና እክል እንዳጋጠመህ ሰምቻለሁ፤ ህመምህ ምንድን ነው?
የልብ ችግር ቀደም ሲል ነበረብኝ፡፡ አሁንም ያው የልቤ ህመም ነው የተባባሰብኝ፡፡ በዚያ ላይ ሁለቱም እግሬ ታፋዬ ላይ አብጦ መራመድ አልቻልኩም፤ ብቻ ተደራርቦብኛል፡፡
ህክምና አላገኘህም እንዴ?
ፖሊስ ሆስፒታል በነፃ መታከም እችላለሁ፤ ግን እዛ ለበሽታዬ መፍትሄ አልተገኘም፤ ላንድማርክም ታክሜያለሁ፤ ውጤት አላገኘሁም፡፡ አሁን ይሄው ኮሪያ ሆስፒታል ዛሬ ሄጄ (ቃለ ምልልሱ ረቡዕ ነው የተደረገው) ውጤት ዘጠኝ ሰዓት ብለውኛል፡፡ እስኪ የሚሆነውን አያለሁ፡፡ እዚህ ካልተቻለ ታይላንድ ባንኮክ ሄደህ ትታከማለህ እያሉኝ ነው፡፡ እግዚአብሄር ያውቃል፡፡
አሁን ሙሉ በሙሉ መራመድ አትችልም?
አልችልም፡፡ በሰው ድጋፍ በምርኩዝ በስንት ችግር ነው የምንቀሳቀሰው፡፡
ስለዚህ ስራ እየሰራህ አይደለማ?
እንዴት አድርጌ… እግሬ አላላውስ ብሎኛል፡፡
በሙዚቃ ህይወት ምን ያህል ጊዜ አሳለፍክ?
ከ60 ዓመታት በላይ ቆይቻለሁ፡፡ በ1940 ዓ.ም ወዳጄነው ፍልፍሉ የሚባል ጓደኛዬና ተፈራ አቡነወልድን አይቼ ነው ወደ ሙዚቃው የገባሁት፡፡ ወዳጄነው ፍልፍሉ ጐበዝ ክላርኔት ተጫዋች ነበር፡፡ ተፈራም ከማዘጋጃ እስከ ብሄራዊ ቴአትርና እስከ ውጭው ዓለም ድረስ ብዙ ታሪክ የሰራ፣ ድንቅ የጥበብ ሰው ነበር፡፡ አሁን ሁለቱም በህይወት የሉም፡፡ መጀመሪያውኑ ዋሽንት መጫወት፣ ሰርግ ላይ መጨፈር እወድ ነበር፡፡ እነተፈራን ሳይ ደግሞ ፍላጐቴ ጨመረና ማዘጋጀ ቤት ገባሁ፡፡ ከዚያ ትንሽ ሰልጥኜ የመንገድ ላይ ታምቡር (ድራም) አስያዙኝ፤ በኋላ እራሴን እያሻሻልኩ ወደ ክላርኔት ተሸጋገርኩ፡፡ ከክላርኔት ወደ ሳክስፎን አሻሻልኩ ማለት ነው፡፡
እዚያው ማዘጋጃ ቤት ተቀጠርክ ማለት ነው?
አዎ! ማዘጋጃ ቤት ውስጥ ከጊዜ ወደ ጊዜ እየተሻሻልኩ ስመጣ፣ ደሞዝ የሁለት የሁለት ብር ጭማሪ ሲደረግ፣ ስንወዳደር ሁሉንም በልጬ ተቀጠርኩኝ፡፡ እነዚያ የበለጥኳቸው ልጆች ተናደው መንገድ ላይ ጠብቀው ደበደቡኝ (ረጅም ሳቅ…)
በጣም ተጐዳህ?
ድብደባው እንኳን እስከዚህም ነው፤ እንደው ነገሩ ነው እንጂ፡፡
የመጀመሪያው ቅጥር ደሞዙ ስንት ቢሆን ነው የሁለት ብር ጭማሪ የተደረገው?
(በጣም እየሳቀ)… ደሞዙማ አስር ብር ነበር፤ መጀመሪያ ስቀጠር፡፡ በውድድሩ እነሱን በልጬ 18 ብር ስለገባሁ አይደለም እንዴ ባልደረቦቼ ደበደቡኝ ያልኩሽ፡፡
ከዚያስ?
ከዚያማ እንዲህ እንዲህ እያልን… በሶስተኛው ዓመት በ1943 ዓ.ም መሆኑ ነው፡፡ ኮሪያ ዝመቱ ተባልን፡፡ በወቅቱ መንግስቱ ነዋይ ኮሎኔል ነበር፤ መጣና፤ “ይህችን ልጅ ተዋት፤ ጥይት አታባክኑ” ብሎ ነገራቸው፡፡ ተስፋዬ ሳህሉ (አባባ ተስፋዬ) ሲዘምት፣ እኔ ቀርቼ በሙዚቃው ቀጠልኩ፡፡ ከተስፋዬ ጋር ሌሎችም ዘምተዋል፡፡ ምክንያቱም እኔ ያን ጊዜ ቀልጣፋና ጐበዝ ነበርኩ፡፡ እነሱ ሰነፍ ስለሆኑ ዘመቱ ማለቴ ግን አይደለም፡፡
ለመሆኑ የሙዚቃ መሳሪያዎቹን ማን አሰለጠነህ?
እኔ ቀደም ብዬ ስትተዋወቂኝ እንዳጫወትኩሽ፣ ሳልማር ያስተማርኩ ነኝ ብዬሻለሁ፡፡ በቀለም ትምህርት እስከ ዘጠነኛ ክፍል ነው የተማርኩት፣ ከዚያ በላይ አልገፋሁም፡፡ የሙዚቃ መሳሪያዎቹን ያስተማሩኝ ግን ነርሲስ ናልቫንዲያን እና ዘልቤከር የተባሉ ሰዎች ናቸው፡፡ ከዚያ እራሴን እያሻሻልኩ በመሄዴ፣ የነርሲስ ረዳት ሆኜ በመምህርነት በርካታ ሰዎችን አስተምሬያለሁ፡፡
በወቅቱ ደራራ ባይሳ የተባለ በኋላ ስሙን ቀይሮ ተድላ ተብሏል፤ እሱ ጐበዝ ሳክስ ተጫዋች ነበር፤ ሁለተኛ እኔ ነበርኩኝ፤ በጥረቴ አንደኛ ሆኜ ረዳት መምህር ሆንኩኝ፡፡
ከማዘጋጃ ቤት በ1948 ወደ ብሄራዊ ቴአትር ቤት ተዛወርክና በርከት ላሉ አመታት እዚያ ሰራህ፣ ከዚያም ወደ ፖሊስ ሙዚቃ ክፍል ገባህ፡፡ እስኪ ሂደቱን አስታውሰኝ?
ልክ ነው በ1948 ብሄራዊ ቴአትር ከገባሁ በኋላ ለ17 አመታት ሰርቻለሁ፡፡ ጥሩ ጊዜ ነው ያሳለፍኩት፡፡ ከዚያ ወደ ፖሊስ የተዛወርኩት የነርሲስ ረዳት መምህር ሆኜ ነው፤ መቼም ፖሊስ ውስጥ እኔና ሂሩት በቀለ ከሌለን ቤቱ አይደምቅም ነበር፡፡ እኔና እሷ ፖሊስን ፖሊስ አሰኝተነው ነው ያለፍነው፡፡ ለበርካታ አመታት አስተማሪም ተጫዋችም ሆኜ ጡረታ እስከወጣሁበት ጊዜ ድረስ አገልግያለሁ፡፡
በ1986 ዓ.ም ነው ጡረታ የወጣኸው አይደለም?
ልክ ነው ከመንግስት ለውጥ ከሦስት አመት በኋላ ነው ጡረታ የወጣሁት፡፡
ፖሊስ ሙዚቃ ክፍል ምክትል መምህር ሆነህ ስትሰራ ዋናው መምህር ነርሲስ ናልቫንዲያን በመሞታቸው፣ ዋና መምህር ሆነህ ነበር፡፡ ለመሆኑ የ18 ብር ደሞዝህ ስንት ደረሰ?
ነርሲስ ሲሞት እኔ ዋና መምህር ሆንኩኝ፡፡ ደሞዙ 800 ብር ነበር፡፡ የእሱ ደሞዝ እንዲከፈለኝ ከተደረገ በኋላ ተስፋዬ አበበ አብሮ ለፍቷል፤ በጀት ውስጥ ይግባ ተባለና የኔ ደሞዝ ለሁለት ተከፍሎ፣ እኔ 600 ብር ሆነ ደሞዜ፡፡
ዶ/ር አርቲስት ተስፋዬ አበበ ናቸው?
አዎ፡፡ እሱንም እንደኔ ረስተውት ነበር፡፡ አሁን አስታውሰው ዶ/ር አድርገውታል፤ እውነት ለመናገር ይገባዋል፡፡ ዘግይተውም ቢሆን ይህን ክብር ስለሰጡት ደስ ብሎኛል፡፡
ጡረታ ከወጣህ በኋላ ሸራተን መስራት እንደጀመርክ ይታወቃል፡፡ ከዚያም ከመቶ በላይ የዓለም አገራትን በስራ መዞርህንም አውቃለሁ፡፡ እስኪ ስለሱ አጫውተኝ?
ልክ ነው ሸራተን ገብቼ ስጫወት የፈረንጅ መአት ይመጣ ነበር፡፡ እኔ እንደነገርኩሽ ብዙ ቋንቋ አልችልም፤ በማህሙድ አህሙድ አስተርጓሚነት ከፈረንጆቹ ጋር ተነጋገርኩና ውጭ መሄድ ጀመርኩ፡፡ ብቻ ምን አለፋሽ… ወደ 104 አገራትን አይቻለሁ፡፡ ጀርመን፣ ፈረንሳይ፣ ሆላንድ፣ አሜሪካ፣ እንግሊዝ… ከመላኩ በላይ ጋር እየዞርን፣ ኢትዮጵያን ኢትዮጵያ አሰኝተናታል፡፡ አሜሪካ እንኳን ሰባት ስቴት ውስጥ ስራዬን አቅርቤያለሁ፡፡ እስራኤልም እንዲሁ… ብቻ አሁን የማስታወስ ችሎታዬ ቀንሷል… ድፍን አለምን ዞሬያለሁ፡፡
የማስታወስ ችሎታዬ ቀንሷል ስትል… ለእርጅና እጅ ልትሰጥ ነው እንዴ?
ኧረ የለም አልሰጥም፤ ገና የ81 አመት አፍላ ጐረምሳ እኮ ነኝ፡፡ በ1927 እኮ ነው የተወለድኩት፡፡
ክፍለሀገር ነው የተወለድከው?
አዎ፡፡ ይፋትና ጥሙጋ ነው፡፡ ልጅ ሆኜ ነው አዲስ አበባ የመጣሁት፤ እስከ ዘጠኝ ተምሬ እንደነገርኩሽ ወደ ሙዚቃው ገባሁ፡፡
ከ100 በላይ የአለም አገራትን ስትዞር መቼም ጥሪት መቋጠርህ አይቀርም ብዬ አስባለሁ፡፡ አሁን ያገኘሁህ ግን በሰዎች እርዳታ ስትታከም ነው፡፡ አሁን ምንም ንብረት የለህም ማለት ነው?
እንዳልሽው ጥሪት ቋጥሬ ነበር፡፡ ለልጆቼም ለጥቂቶቹ ላዳም ገዝቼ ሰጥቼ ነበር፡፡ መለስተኛ ቤትም አለኝ፡፡ ነገር ግን ባለቤቴም እኔም ታመን ያልሄድንበት ሆስፒታል፣ ያልታከምንበት ሀኪም ቤት የለም፡፡ ግን ገንዘቤን አሟጥጬ ከመጨረስ በቀር መፍትሄ አላገኘሁም፤ በመጨረሻ ከስድስት ወር በፊት ባለቤቴ አረፈች፡፡ (በጣም ትካዜ ውስጥ ገባ) ገንዘቤ ሲያልቅ መልሼ ፖሊስ ሆስፒታል አስገብቻት ነበር፡፡ የልብ ህመም ነበረባት፤ አልዳነችም፡፡ ምን አለፋሽ… ከአምስት ሚሊዮን ብር በላይ አጠራቅሜ ነበር፤ አሁን ይሄው መላኩ ነው እየደገፈኝ ያለው፡፡
ብዙ ልጆች እንዳሉህ ሰምቻለሁ፤ አይረዱህም?
ዘጠኝ አካባቢ ልጆች አሉኝ፤ የቁጥራቸው መብዛት ፋይዳ የለውም፡፡ በአጭሩ ለራሳቸውም በቂ ኑሮ እየኖሩ አይደለም፡፡
ከሸራተን ስራ ያቆምከው ለምን ነበር?
ሸራተን እየሰራሁ እንዳልኩሽ ለስራ ብዙ ጊዜ ወደ ውጭ እወጣ ነበር፡፡ “እዚህ እየሰራህ እንዴት ውጭ ሄደህ አንድና ሁለት ወር እየቆየህ ትመጣለህ?” አሉኝ፡፡ ታዲያ ስራ ላልሰራ ነው፤ ከፈለጋችሁ ተውት እንጂ ውጭ መሄዴን አላቆምም ስል፣ ለሼህ አላሙዲን ነገሩት እና አቀያየሙን፡፡ እንደውም እሱ የገዛልኝን ሳክስፎን እንመልስልሃለን ብለው ወስደው ሸጡት፡፡
እነማን ናቸው የሸጡት?
የኔ ልጅ ተይው እከሌ ነው እከሌ ነው ማለቱ ጥቅም የለውም፡፡ ስም ለመጥራትም ያስቸግራል፡፡ ብቻ ያልኩሽ ሆኗል፡፡ እኔም በጣም ተቀየምኩኝ፡፡
እና አሁን ሳክስፎን የለህም?
ኧረ ደንበኛው ሳክስፎን ነው ያለኝ፡፡ ክላርኔትም አልቶም አለኝ ሶስትና አራት መሳሪያ ነው የምጫወተው፡፡ ይሄው ሶስት አመት ስታመም ተረስቼ ቀረሁ፤ ጤናው ቸገረኝ እንጂ መሳሪያው አለኝ፡፡ አሁን ለብሄራዊ ቴአትር 60ኛ አመት በዓል እኔና መርአዊ ስጦት በተቻለን መጠን አንድ ሙዚቃ ለመጫወት አስበናል፤ ከተሻለኝ ማለቴ ነው፡፡ ያው እሱም ልቡን ያመዋል እንደሚታወቀው፡፡
አሁን ከማን ጋር ነው የምትኖረው? ማንስ ነው የሚጦርህ?
አንድ ሴት ልጅ አለችኝ፡፡ እሷ ብቅ እያለች ታየኛለች፤ በቃ ከሰራተኛ ጋር ነው የምኖረው፡፡
የገቢ ምንጭህ ምንድነው?
ቤት አለኝ ብየሽ የለም፤ ሁለት ትንንሽ ክፍሎች አከራያለሁ፤ ከእነሱ ወደ አንድ ሺህ ብር አካባቢ አገኛለሁ፡፡ ጡረታዬ አሁን በጭማሪው ሁለት መቶ ብር ተጨምሮልኝ ወደ አምስት መቶ ከፍ ብሏል፤ እሷን እሷን እያደረግሁ ነው የምኖረው፡፡
ለህክምና ባንኮክ ያልከውስ…?
እንኳን ባንኮክ ሄጄ የምታከምበት አሁን ሃኪም ቤት የምመላለስበትንና የምታከምበትን እንኳን የሚከፍልልኝ ይሄው መላኩ በላይ ነው፡፡ እንግዲህ ፈጣሪ ያውቃል፡፡
ብዙዎቹ የአገር ባለውለታዎች በህመምና በገንዘብ ማጣት ሲቸገሩ ብዙ አያገኙም፤ “ሲሞቱ ግን ቀብራቸው ይደምቃል” ይባላል፡፡
ልክ ነው፡፡ እኔ አንድ የምወደው አባባል አለኝ፤ “ከሞተ ጀነራል የቆመ ወታደር ይሻላል” የሞተን ሰው ጀነራል ከማድረግ፣ ለቆመው ወታደር እንክብካቤ መስጠት ተገቢ ይመስለኛል፡፡ ምክንያቱም አንድ ሰው ከሞተ በኋላ ጀነራል፣ ሚኒስትር፣ ደጃዝማች እያሉ ማሞካሸትና መካብ የወሬ ጋጋታ ብቻ ነው የሚሆነው፡፡ ስለዚህ ያን ያህል ክብር ከሰጡት በቁም የሚያስፈልገውን እንክብካቤ ማድረግ ተገቢ ነው፡፡ እኔም አሁን ታምሜ ብረሳም ሲሻለኝ ብቅ ብዬ ህዝቡን አለሁ እለዋለሁ፡፡ ህዝቡ ራሱ እንደሚያሳክመኝ አምናለሁ፡፡ እዚያ ከመድረሴ በፊት ግን ሁሉም በየእምነቱ እሱ እንዲምረኝ ይፀልይልኝ፡፡
እስኪ ማዘጋጃም ብሄራዊ ቴአትርም ፖሊስ ክበብም ስትሰራ ያጋጠመህና የማትረሳቸው ፈገግ የሚያሰኙ፣ የሚያሳዝኑ ገጠመኞች ካሉህ አጫውተኝ…
አንዱ ቀደም ብዬ የነገርኩሽ ነው፡፡ ማዘጋጃ ቤት ተወዳድረን ሳሸንፋቸውና ደሞዜ 18 ብር ሲገባ ባልደረቦቼ የደበደቡኝን አልረሳውም፡፡ እንደውም ሳስታውሰው ያስቀኛል፡፡ ሌላው ፖሊስ ሙዚቃ ክፍል ውስጥ እያለሁ የሚሊታሪ ልብስ እለብስ ነበር፤ ቅጥሬ ግን በሲቪል ነው፡፡ የሚሊታሪውን ልብስ ስለብስ ግን ከጀነራሉ የበለጠ ያምርብኛል፡፡ ሲያዩ የማእረግ ምልክት የለውም፤ ምንድነው ማእረግህ፤ “ኮሌኔል ባሻ” እላለሁ፡፡ ሌላውም ሲጠይቀኝ፤ “ኮሎኔል ባሻ” እላለሁ፡፡ ይሄ በሰራዊቱ ውስጥ የሌለ ማእረግ ነው፤ ግን እነሱ ይኑር አይኑር አያውቁትም፡፡
 ይሄን የምለው ናቅፋ አልጌና እና አውራሮ ስሄድ ነው፡፡ ሌላ ጊዜ ሲጠይቁኝ፤ “አሁንማ ጀነራል ባሻ ሆኛለሁ” ስል አንድ ችኩል የሆነ ኮሎኔል አያሌው አበበ የሚባል አለቃ ነበረኝ፤ “ዝም በሉት፤ እንዲህ የሚባል ማእረግ የለም፤ እሱ ሲቪል ነው” ብሎ አዋረደኝ እልሻለሁ (ረጅም ሳቅ…)
ታዲያ ያኔ ጦር ሰራዊቱ አዲስ ማእረግ የመጣ እየመሰለው፤ “ጀነራል ባሻ” እያለ ወታደራዊ ሰላምታ ገጭ ያደርግልኛል፡፡ እኔም ምላሹን እሰጥ ነበር፡፡
አንዴ ደግሞ ሱዳን ሄጄ ሙቀቱ ሲያስቸግረኝ ሻወር ለመውሰድ ገንዳውን ውሃ ከፍቼ እየሞላሁ፣ እዚያው ባለሁበት እንቅልፍ ጭልጥ አድርጐ ወሰደኝ፡፡ ውሃው ከገንዳው አልፎ እስከ ውጭ ድረስ ይፈሳል ለካ፡፡ ሰራተኞቹ እንደምንም በመስታወት ተንጠራርተው ሲመለከቱ፣ ውሃው ውስጥ ተኝቻለሁ፡፡ “ወፍራም ሰው ገንዳ ውስጥ ሞቷል” ብለው መጮህ ጀመሩ፡፡ ከዚያ በሩን በሃይል ክፍት ሲያደርጉት፣ ብንን ብዬ ተነሳሁ፡፡ “አስደነገጥከን እኮ” ብለው ጮሁ፤ ይሄ ብሄራዊ ቴአትር ስሰራ ሱዳን ሄጄ ነው የተከሰተው፡፡
አሁን ከድሮ ጓደኞችህ ጋር ትገግኛለህ… ትጠያየቃለህ?
አዎ ከድሮ ጓደኞቼ ጋር አልፎ አልፎ እንጠያየቃለን፤ በተለይ ከመርአዊ ስጦት ጋር፡፡ ከግርማ፣ ከተስፋዬ አበበ፣ ከአፈወርቅ ጋር እንገናኛለን፡፡ ማህበርም አለን፤ በብሄራዊ ቴአትር በኩል፡፡ በግልም የሽማግሌዎች ማህበር አለን፡፡ እኔ ስላመመኝ ነው እንጂ በየወሩ ቅዳሜ ቅዳሜ እንገናኝ ነበር፡፡
በወጣትነትህ ምን አይነት ባህሪ ነበረህ? ለመጀመሪያ ጊዜ ትዳር የመሰረትከው በቅርብ ካረፉት ባለቤትህ ነው ወይስ?
እኔ በወጣትነቴ ሌላ ሚስት ነበረችኝ፡፡ የመጀመሪያው ትዳሬ ጥሩ አልነበረም፡፡ አሁን በቅርብ ካረፈችው ባለቤቴ ጋር ከተጋባን 55 አመታችን ነው፡፡ ከመጀመሪያው ትዳሬ ሦስቱ ልጆች ቢወለዱም አብዛኛዎቹ ከዚህችኛዋ የተወለዱ ናቸው፡፡ የጨዋ ቤተሰብ ልጅና መልካም ሴት ነበረች፤ መልክና ቁመናዋም ሌላ የሚያሳይ አልነበረም፡፡ ከሷ በኋላ ወደዚህም ወደዚያም ሳልል፣ በሰላምና በፍቅር ነው የኖርነው፤ ሞት ለያየን እንጂ፡፡ ብቻ ነፍሷን ይማረው፡፡በኃይለስላሴ ዘመነ መንግስት፣ በደርግ አሁንም በኢህአዴግ … በሦስት መንግሥታት ኖረሃል፡፡ በእነዚህ ሦስት መንግስታት የሙዚቃ ሁኔታ… አጠቃላይ የስርአቶቹ ሂደት በአንተ አስተያየት ምን ይመስላል?
እኔ እንግዲህ ሽማግሌ እንደመሆኔ የአድርባይነት ወሬ አላወራሽም፡፡
 ይህችን አገር በስልጣኔውም ሆነ በሁሉ ነገር መሰረት ያስያዟት አፄ ምኒልክ እና ኃይለስላሴ ናቸው፡፡ በኋላ መንግስቱ ኃይለማሪያም የሚባል አገር አጥፊ መጥቶ፣ አገሪቱን እንዳልነበረች አደረጋት፡፡ አሁን ብዙ ሰው “መንግስቱ የሀገር ፍቅር አለው” ብሎ ይከራከራል፤ አገሩን የሚወድ ሰው ያንን ሁሉ የአገሪቱን ምሁራን ሰብስቦ ይጨርሳል እንዴ? እሱ የሚወደው ራሱንና ስልጣኑን ነበር፡፡ ከዚያ አገር አጥፊ መቼም አንደኛውን ኢህአዴግ ይሻላል፡፡ እንግዲህ ኢህአዴግንም ሆነ ደርግን ብወድም ባልወድም መብቴ ነው ግን ኢህአዴግንም የምነቅፍበት ብዙ ጐኖች አሉኝ፡፡
ለምሳሌ?
ለምሳሌ ኤርትራን አስገንጥሎ አገሪቱን የባህር በር በማሳጣቱ፣ አንቀፅ 39ን አምጥቶ ህዝብ በመከፋፈሉ ቅር እሰኛለሁ፡፡ ከተማዋም ብትሆን በእቅድ ብትገነባ ጥሩ ነው፤ ህዝቡ አሁን በመቶ ብር አንድ ፌስታል እቃ አይሸምትም፤ ነፃ ገበያ እየተባለ ማንም የሚፈነጭባት አገር ሆናለች፡፡ ይሄ ይሄ ቢስተካከል ኢህአዴግ ጥሩ ይሆን ነበር፡፡  
ምህረቱን ይስጥህ… ጋሽ ጌታቸው፡፡
አመሰግናለሁ፡፡ እናንተም አስታውሳችሁኝ ስለመጣችሁ አመሰግናለሁ፡፡ አሁን አሞኛል እኔ ያቅሜን ያህል አገሬንና ህዝቤን አገልግያለሁ፤ ህዝቡ ቢፈልግ ያሳክመኝ፤ አለበለዚያ ስሞት ይቅበረኝ፡፡ ይሄው ነው አመሰግናለሁ፡፡       


     ቅልጥጥ ያሉ የሀብታም ገበሬ ልጅ ናቸው፡፡ ሐጂ አባመጫ አባደጋ፡፡ አባታቸውም ሆኑ አያታቸው በርካታ ጋሻ የቡና መሬት የነበራቸው ሀብታሞች እንደነበሩ አጫውተውናል፡፡ ሐጂ አባመጫ አሁን የሚኖሩት አጋሮ ከተማ ውስጥ ቢሆንም የተወለዱት ከከተማው ትንሽ ወጣ በምትል ኪሎሌ በተባለች የገጠር መንደር ነው፡፡
ሐጂ አባመጫ እድሜያቸውን በትክክል አያውቁትም፡፡
74 ወይም 75 ዓመቴ ነው ቢሉም ከዚያ በላይ እንደሚሆናቸው መገመት ይቻላል፡፡ አባታቸው በልጅነት ቢሞቱባቸውም አቶ ሺበሺ ገብረየስ የተባሉ ሞግዚት ተሹሞላቸው በቅምጥል ነው ያደጉት፡፡ አገር መጐብኘት የጀመሩት በልጅነታቸው ሲሆን የኢትዮጵያ አየር መንገድ የሚበርባቸውን ከተሞች ሁሉ ማየትና መጐብኘታቸውን ይናገራሉ፡፡ ከጂማ ጐሬ፣ ከጂማ አዲስ አበባ፣ ከጂማ ጋምቤላ፣ ከጂማ አስመራ፣ ከጂማ… ብዙ ቦታዎችን ጐብኝተዋል፡፡ ሐጂ ወደ ሳዑዲ የሄዱትም በልጅነታቸው እንደሆነ አውግተውናል፡፡ከቦታ ቦታ የሚዘዋወሩት በአውሮፕላን ቢሆንም፣ የዚያን ጊዜ አውሮፕላኖች አይመቹም፡፡ ቡና፣ ቆዳ፣ በርበሬ፣ ቅመማ ቅመም፣… ይጫንባቸዋል፡፡ ሰውና ዕቃ የሚጫነው አንድ ላይ ነበር፡፡ ይህ ነገር ለወጣቱ ሐጂ አባመጫ አልተመቻቸውም፡፡ “የራሴ አውሮፕላን ቢኖረኝ!” እያሉ ማሰብ ጀመሩ፡፡
በአንድ ወቅት ተከሰው አዲስ አበባ መጥተው ነበር፡፡ ከራስ አደፍርስ 20 ጋሻ የቡና መሬት ገዝተው ነበር፡፡ ሳይገብሩ ብዙ ይቆያሉ፡፡ ራስ አደፍርስ ከስሰው አዲስ አበባ አስጠሯቸው፡፡ ሞግዚታቸውን አቶ ሺበሺ፣ ቅጥረኛ ፀሐፊዎቻቸውን፣ ሌሎች አጃቢዎችንም አስከትለው መጡ፡፡ ራስ አደፍርስ “የግብር አልከፈላችሁ፣ ማር አልጫናችሁ… ምንድነው ነገሩ?” ብለው ተቆጡ፡፡
ጥፋታቸውን አምነው፣ ግብሩንም ለመክፈል ተስማምተው ተመለሱ፡፡የግል አውሮፕላን እንዲኖራቸው የመፈለግ ጉጉታቸው እየጨመረ ሄዶ ለመግዛት ወሰኑ፡፡ እንዳጫወቱን፤ አጋሮ እንደተመለሱ በ13 ዓመታቸው፤ ማርትሬዛ በስልቻ ሞልተው ብቻቸውን አዲስ አበባ መጥተው ራስ አደፍርስን “አውሮፕላን መግዛት እፈልጋለሁ” አሏቸው፡፡ ራስም ግራ በተጋባ ስሜት፤ “ለመሆኑ አውሮፕላን በስንት ብር ነው የምትገዛው?” በማለት ጠየቋቸው፡፡ ሐጂ አባመጫም፤ “ጠይቀህ ንገረኝ እንጂ!” ሲሉ መለሱላቸው፡፡ ወሬው ራስ መስፍን ስለሺ ጋ ደረሰና በንዴት ጦፉ፡፡“ብሩን አምጣ፡፡ እኔ እገዛልሃለሁ” በማለት የያዙትን ገንዘብ ተቀበሏቸው፡፡ በዚህ ብቻ አላበቁም፡፡ “ጨምር!” አሏቸው፡፡ “አውሮፕላኑን ሳላይ እንዴት እጨምራለሁ? እኔ ከዚህ በላይ የለኝም” አሉ ሐጂ አባመጫ፡፡ ራስ መስፍን፣ “እንዴት አውሮፕላን ለመግዛት ትነሳለህ? ወንጀል መሆኑን አታውቅም?” በማለት ሊያስሯቸው ፈለጉ፡፡ሐጂ “እኔ ውንጀላ መሆኑን አላወኩም” አሉ፡፡ ራስ አደፍርስና የቢትወደድ እንዳልካቸው መኮንን አባት ሽምግልና ገቡና “አሁን ይኼ ልጅ ምኑ ይታሰራል? ወጣት ነው፤ የመግዛት ፍላጐት አደረበት፣ ለመግዛት ተነሳ፡፡ ከዚህ ጥፋ ብሎ ማባረር ነው እንጂ ምኑ ይታሰራል?...” በማለት ሸመገሉ፡፡ በዚህ አይነት ሐጂ አባመጫ ከእስር ድነው፣ ሉክስ (አዲስ) ላንድሮቨር ገዝተው ወደ አገራቸው ተመለሱ፡፡ሐጂ አባመጫ ለቤተሰባቸው ሁለተኛ ልጅ ናቸው፡፡ ታላቃቸው ደግሞ ሴት ናቸው፡፡ ስለዚህ በተለያየ ቦታ ያለውን የቡና እርሻ የሚያስተዳድሩት እሳቸው ናቸው፡፡ በአንድ ወቅት ከወረሱት ሌላ በግላቸው 12 ጋሻ መሬት ቡና ነበራቸው፡፡ ታዲያ ቡና ተለቅሞ ሲሸጥ በሺዎች ኩንታል ነበር፡፡
“የቡና ዋጋ እንዳሁኑ ቢሆን ኖሮ አውሮፕላኑም ይገዛ ነበር” በማለት ቀልደዋል፡፡ ታዲያ ምን ያደርጋል? አዱኛ ብላሽ! እንደሚባለው አብዮት መጣና ሙልጫቸውን አስቀራቸው፡፡
አሁንም ግን አጋሮ ከተማ ውስጥ ቦታ ገዝተውና ቤት ሰርተው እየኖሩ ነው፡፡ ኑሮአቸው ጥሩ ነው፡፡ ቤታቸው ሰፊ ሲሆን ሁለት ግቢ አለው፡፡ አራቱ ወንዶች ልጆቻቸው አሜሪካ ይኖራሉ፡፡ ሁለት ሴቶች አዲሳባ አሉ፡፡ ሌሎቹ አጋሮ ከተማ አብረዋቸው ይኖራሉ፡፡

      ወ/ሮ ካሙላ ፊጣ ሦስት ልጆቿን በሰላም ነው የተገላገለችው፤ ሁለቱን በቤት አንዱን በጤና ጣቢያ፡፡ አራተኛው ፅንስ ግን ለመወለድ አልታደለም፡፡ 4 ወር ሲሆነው በሆዷ ሞቶ ደም ስለፈሰሳት ወ/ሮ ካሚላ ወደ ሰከቻ ክሊኒክ ተወሰደች፡፡ የክሊኒኩ ባለሙያዎች አይተው ከአቅማቸው በላይ ስለሆነ፣ ሪፈር ጽፈው፣ አምቡላንስ ጠርተው ወደ በደሌ ሆስፒታል ላኳት፡፡ የሆስፒታሉ ባለሙያዎችም በሆዷ የሞተውን ሽል በመሳሪያ አውጥተውላት እፎይቷ ሰጧት፡፡
የሦስት ልጆች እናት የሆነችው ወ/ሮ ያማቱ ናስር፤ ወደ በደሌ ሆስፒታል የመጣችው አራተኛ ልጇን ለመገላገል ነው፡፡ ወ/ሮ ያማቱ እርግዝናዋን በአካባቢዋ ባለ ጤና ጣቢያ ስትከታተል ነበር፡፡ ምጥ ስለመጣባት ወደ ባሌ ከተማ ሆስፒታል መጥታ አልጋ ላይ ሆና መውለጃዋን እየተጠባበቀች ነው፡፡ በሆስፒታሉ የማዋለጃና የመቆያ ክፍሎች ብዙ እናቶች አሉ፡፡
ሁሉም ወላዶች አልጋ ላይ ተኝተዋል፡፡ በደሌ ቢራ ምስጋና ይግባውና ሁሉም እናቶች አልጋ ላይ መውለድ ችለዋል፤ ብለዋል - የሆስፒታሉ ሥራ አስኪያጅ አቶ ታመነ ወርቅነህ፡፡
አቶ ታመነ መንግሥት በበደሌ ከተማ ያሰራው ሆስፒታል 64 አልጋዎች እንዳሉት ጠቅሰው፣ የሆስፒታሉ አስተዳደር 20 ክፍሎች ጨምሮበት፣ የአልጋዎቹ ቁጥር 84 መድረሱን ተናግረዋል፡፡ ነገር ግን ሆስፒታሉ አገልግሎት የሚሰጠው በ10 ወረዳ ለሚገኙ 710, 900 ሰዎች ስለሆነ በቂ አይደለም፡፡ ባለፈው ዓመት 1,652 እናቶች ናቸው በሆስፒታሉ የተገላገሉት፡፡
በአማካይ በየቀኑ 5 ሴቶች ይወልዱ ነበር ማለት ነው፡፡ ሁለትና ሦስት የሚወለድበት ቀን ቢኖርም 15 ሴቶች የሚወልዱበት ጊዜም አለ፡፡ አልጋ ሲጠፋ መሬት ላይ የሚወልዱ እናቶች ነበሩ፡፡ አሁን ማስፋፊያው ከተሰራ በኋላ መሬት የምትወልድ እናት የለችም፡፡ እናቶችን ከመሬት አንስተን አልጋ ላይ ማስተኛት ችለናል ብለዋል፡፡
በደሌ ቢራ አ.ማና ሄኒከን አፍሪካ ፋውንዴሽን በበደሌ ከተማ ሆስፒታል ውስጥ በ5.6 ሚሊዮን ብር ያሰሩት የማስፋፊያ ፕሮጀክት ባለፈው ሳምንት የተመረቀ ሲሆን 12 አዲስ የእናቶች ማዋለጃና 24 የሕፃናት ማቆያ ክፍሎች ያላቸው ሁለት ብሎኮች በ3.1 ሚሊዮን ብር አስገንብቷል፡፡ ለህክምናና ለላብራቶሪ መሳሪያዎች፣ ለጨቅላ ህፃናት ማቆያ ኢንኩቤተር፣ ለሥልጠና፣ … 2.5 ሚሊዮን ማውጣቱን አቶ ታመነ አስረድተዋል፡፡ ቀደም ሲል ከክፍሎች ጥበት የተነሳ የቤተሰብ ምጣኔ፣ ኤችአይቪ ከእናት ወደ ልጅ እንዳይተላለፍ፣ ክትባትና ከወሊድ በኋላ ክብካቤ የሚሰጠው በአንድ ክፍል ውስጥ ነበር፡፡ የሄይኒከን ቢራ አ.ማ ማኔጂንግ ዳይሬክተር ሚ/ር ጌሪት ቫን ሉ፤ “የማስፋፊያው ፕሮጀክት ለእናቶችና ከ5 ዓመት በታች ላሉ ህፃናት፣ የተሻለና ጥራት ያለው አገልግሎት መስጠት እንደሚያስችል እናምናለን” ብለዋል፡፡
ሚ/ር ቫን ሉ ባለፉት 4 ዓመታት ፋብሪካውን ለማዘመንና ደረጃውን ከፍ ለማድረግ 100 ሚሊዮን ብር ማውጣታቸውን ጠቅሰው፤ ለአንድ ሄክቶ ሊትር ቢራ ጠመቃ ያስፈልግ የነበረውን 11 ሊትር ውሃ ወደ 5.5 ሄክቶ ሊትር ማውረዳቸውን እንዲሁም ለቢራ ጠመቃ የተጠቀሙበትን ውሃ ለማጣራትና ከብክለት ነፃ ለማድረግ፣ 23 ሚሊዮን ብር ማውጣታቸውን ተናግረዋል፡፡ በደሌ ቢራ በቀረጥ ለመንግስት የሚያስገባው ገቢ በአራት እጥፍ ያህል ማደጉን የጠቀሱት ማኔጂንግ ዳይሬክተሩ፣ በ2000 ዓ.ም 71.9 ሚሊዮን የነበረው ታክስ፤ በ2006 ዓ.ም 280.9 ሚሊዮን ብር መድረሱን ገልጸዋል፡፡ ለቢራ ጠመቃ በጣም አስፈላጊ የሆነውን ገብስ 48 ከመቶ ከሀገር ውስጥ እንደሚያገኙ ጠቅሰው፣ በቀጣይ ዓመታት ከውጭ የሚመጣውን 20ሺህ ሜትሪክ ቶን ገብስ በአገር ውስጥ ለማምረት፣ ከ20ሺህ ገበሬዎች ጋር እየሰሩ መሆኑን ሚ/ር ጌሪት ቫሉ አስረድተዋል፡፡

Saturday, 17 October 2015 09:44

የዘላለም ጥግ

• ትላቁ ክብራችን ጨርሶ አለመውደቃችን
ሳይሆን፤ በወደቅን ቁጥር መነሳታችን
ነው፡፡
ኮንፉሺየስ
• ታሪክ፤ ጥቂት ኦሪጂናሌና ብዙ ቅጂዎች
የሚገኙበት የስዕል ጋለሪ ነው፡፡
አሌክሲስ ዲ. ቶክኪውቪሌ
• ታሪክ ምንድን ነው? ሰዎች
የተስማማሙበት ተረት አይደለም?
ናፖሊዮን ቦናፓርቴ
• በውስጡ እየኖርክበት ሳለ፣ ታሪክ ፈፅሞ
ታሪክ አይመስልም፡፡
ጆን ደብሊው ጋርድነር
• ታሪክ፤ ሊወገዱ የሚችሉ ነገሮች ድምር
ውጤት ነው፡፡
ኮንራድ አዴናውር
• ታሪክ፤ ስምምነት ላይ የተደረሰበት
የውሸት ስብስብ ነው፡፡
ናፖሊዮን ቦናፓርቴ
• ታሪክ፤ ትልቅ የቅድምያ ማስጠንቀቂያ
ስርአት ነው፡፡
ኖርማን ከዝንስ
• ታሪክን እንደ ህብረተሰብ ዝግመተ-ለውጥ
መመልከት አለባችሁ፡፡
ዣን ችሬቲን
• የታሪክ ባለሙያ፡- ያልተሳካለት የረዥም
ልብወለድ ፀሃፊ ነው፡፡
ኤች.ኤል.ሜንኬን
• እግዚአብሄር ያለፈውን መቀየር
ባይችልም፤ የታሪክ ባለሙያዎች ግን
ይችላሉ፡፡
ሳሙኤል በትለር
• የእኔ ትልቁ ጠላቴ ጊዜ ነው፡፡
ኢቪታ ፔሮን
• የቀድሞ ታሪካቸውን፣ አመጣጣቸውንና
ባህላቸውን የማያውቁ ህዝቦች፣ ስር
እንደሌለው ዛፍ ናቸው፡፡
ማርከስ ጋርቬይ
• በሰው ልጅ ታሪክ ድንቁርና ከእውቀት
የተሻለበትን ዘመን ጨርሶ አላውቅም፡፡
ኔይል ዲግራሴ ታይሰን
• ቤተ-መፃህፍት የሃሳቦች ማዋለጃ ክፍል
ነው፤ ታሪክ ነፍስ የሚዘራበት ስፍራ፡፡
ኖርማን ከዝንስ
• የነፃ ሰዎች ታሪክ ጨርሶ በእድል የተፃፈ
አይደለም፤ በምርጫ እንጂ፡፡ በራሳቸው
ምርጫ!!
ድዋይት ዲ. አይዘንሃወር
(ስለ ታሪክ)

በድህነትና በመስኖ እርሻ እጦት ሳቢያ፣ ከ8 ሚ. በላይ ኢትዮጵያዊያን ለረሃብ በተጋለጡበት አመት!

   በመስኖ እርሻ፣ በፋብሪካ፣ በኤሌክትሪክ እጦት... በድህነት ላይ የምትገኝ አገር ላይ፤ ሂዩማን ራይትስ ዎች “መስኖና ፋብሪካ በዛ” የሚል አለማቀፍ ዘመቻ ሐሙስ እለት ጀምሯል።
ተቋሙ ያሰራጨው፣ ባለ 103 ገፅ ሪፖርት፣ በፓሪስ ለሚካሄደው ‘የአካባቢ ጥበቃ’ ጉባኤ ታስቦ የተዘጋጀ, የዘመቻ፣ ሰነድ እንደሆነ ተጠቅሷል። “አለማቀፍ የአካባቢ ጥበቃ ዘመቻ”!
የዘመቻው ዋናው ርዕሰ ጉዳይ ደግሞ፣ ኢትዮጵያን መወንጀል ነው - ‘በኬንያ ለሚገኘው ቱርካና ሐይቅ ተቆርቋሪ ነኝ’ በማለት። የኢትዮጵያ ግድብ፣ መስኖ እና ፋብሪካ፣... የቱርካና ሐይቅን ይጎዳሉ በማለት ውግዘቱን ይዘረዝራል።
እስካሁን የሐይቁ መጠን እንዳልቀነሰ ግን፣ በሪፖርቱ ውስጥ አልተገለፀም።
በኬንያ የተካሄደው የግድብ ግንባታና የመስኖ እርሻም፣ አንድም ጊዜ በሪፖርቱ አልተነሳም። ታዲያ ለምን፣ የኢትዮጵያ ግድብ፣ ፋብሪካና መስኖ ላይ፣ አለማቀፍ ዘመቻ ይካሄዳል? ለዚያውም፣ የፋብሪካና የመስኖ እጥረት ባለበት አገር ላይ ነው፣ የውግዘት ዘመቻ የተከፈተው።
የአካባቢ ጥበቃ ዘመቻ... ትርጉም
“የአካባቢ ጥበቃ”... ምን ማለት እንደሆነ እስካሁን ያልተገነዘቡ ሰዎች፣ ትርጉሙን... ሂዩማን ራይትስ ዎች ካዘጋጀው የዘመቻ ሰነድ፣ በግላጭ መረዳት ይችላሉ። “የአካባቢ ጥበቃ” ማለት፣... ችግኝ መትከልና የአካባቢን ንፅህና መጠበቅ... ማለት አይደለም።
የመስኖ እርሻንና ኢንዱስትሪን መቃወም ማለት ነው - የአካባቢ ጥበቃ ማለት። ነባር የአካባቢ ገፅታ፣ የሰው እጅ ሳያርፍበት ‘ተጠብቆ’ እንዲቀጥል፤ ነባሩ ኋላቀር አኗኗር ሳይለወጥና ሳይሻሻል መቀጠል አለበት። በተለይ ግድብና የመስኖ እርሻ፣ ኢንዱስትሪና የፋብሪካ ምርት... ዋና ጠላቶች ናቸው። በሌላ አነጋገር፣ ዋናው ‘የአካባቢ’ ጠላት፣ ‘ሰው እና የሰው ስራ’ ናቸው።
እንግዲህ፣ ለሰዎች መብት እከራከራለሁ የሚለው ሂዩማን ራይትስ ዎች፣ አሁን “የአካባቢ ጥበቃ” ፊታውራሪ በመሆን ነው - አለማቀፍ የዘመቻ ሰነድ ያሰራጨው።
ሰነዱ፣ በገፅ 12፣ እንዲህ ይላል።    
ኢትዮጵያ፣ ባለፉት አመታት፣ ትላልቅ የግድብ ግንባታዎችን፣ እንዲሁም ለስኳርና ለጥጥ ምርት፣ የመስኖ እርሻዎችን ስታዘጋጅ ቆይታለች። እነዚህ ፕሮጀክቶች፣ ወደ ቱርካና ሐይቅ የሚደርሰውን ውሃ እጅጉን ይቀንሱታል። የመስኖ እርሻዎቹ፣ የወንዙን 50 በመቶ ያህል ውሃ ሊቀንስ ይችላል።...
ለዚህ የሪፖርቱ አባባል፣ አንድ ጥናት በማስረጃነት ተጠቅሷል - አንድ ጥናት!
ለዚያውም፣ ይሄው ጥናት ራሱ፣ የኢትዮጵያ የመስኖ ፕሮጀክቶች፣ ወደፊት የወንዙን 26% ያህል ለእርሻ ሊያውል ይችላል ነው የሚለው። የሂዩማን ራይትስ ዎች፣ ይህንን አድበስብሶ ያልፋል። ይህም ብቻ አይደለም። ከኦሞ ወንዝ ውሃ ውስጥ፣ ሰላሳ በመቶ ያህሉ፣ ወደ ግድብ ሳይገባ በቀጥታ ወደ ቱርካና ሐይቅ እንደሚገባ ሳይገለፅ ታልፏል።
ለነገሩ፣ ወደ ጊቤ ግድብ ከሚገባው ውሃ ውስጥም፣ በአብዛኛው ለመስኖ ሊውል አይችልም። ምክንያቱም፣ መፍሰስ አለበት - ኤሌክትሪክ ለማመንጨት። ከፈሰሰ ደግሞ፣ መድረሻው ቱርካና ሐይቅ ነው። ይህም እውነታ፣ በሂዩማን ራይትስ ዎች ሳይጠቀስ ታልፏል።
ደግሞስ፣ ኢትዮጵያ ከኦሞ ወንዝ፣ 50 በመቶ ያህሉ ለመስኖ ብትጠቀም ችግሩ ምንድነው? እንዴት ይወገዛል?
ሂዩማን ራይትስ ዎች ግን፣ ከማውገዝም አልፎ፣ ለአለማቀፍ ዘመቻ ተነስቷል - ሌሎችም እንዲያወግዙ።  
ለምሳሌ፣ “የኬንያ መንግስት፣ የኢትዮጵያ የግድብ ግንባታን በይፋ መቃወም ትቷል” ሲል ወቅሷል - ተቋሙ። (ገፅ 64)
የቱርካና አካባቢ አስተዳደርም፣ በአብዛኛው በዝምታ የሚመለከትና የመስኖ ልማት እቅድ ውስጥ ስለ ሀይቁ ምንም አይናገርም።
ለጊቤ3 ግድብ ግንባታ፣ ብድር እንዳይገኝ በየአቅጣጫው በተካሄደ ዘመቻ ሳቢያ፣ ቀደም ሲል ቃል ገብተው የነበሩት የአፍሪካ ልማት ባንክና የአውሮፓ ኢንቨስትመንት ባንክ ብድር ለመከልከል መወሰናቸውን ታስታውሱ ይሆናል። ጭራሽ፣ ኬንያንና ኢትዮጵያን የሚያገናኝ የኤሌክትሪክ መስመር ለመዘርጋት፣ የአለም ባንክ ብድር መስጠቱንም ተቃውሟል - የሂዩማን ራይትስ ዎች ሰነድ።
በዚህ መሃል...    
በቱርካና አካባቢ፣ ከፍተኛ የነዳጅ ዘይት ክምችት፣ እንዲሁም የኬንያን የውሃ ፍላጎት ለ70 ዓመታት ሊያሟላ የሚችል የከርሰ ምድር ባህር እንደተገኘ ሪፖርቱ ይጠቅሳል። በዚህ የነዳጅና የውሃ ክምችት ላይ፣ ማንም ኢትዮጵያዊ የይገባኛል ጥያቄ ያቀርባል ተብሎ አይጠበቅም። የቱንም ያህል በነዳጅና በውሃ እጥረት ብንቸገር፣ ኬንያ ውስጥ የሚመነጭ ውሃና ነዳጅ ላይ፣ ጥያቄ እናነሳለን? ኬንያዊያን ይህንን አይጠብቁም። ሙሉ ለሙሉ ራሳቸው ቢጠቀሙበት፣ ውንጀላ አይሰነዘርባቸውም።
ታዲያ፣ ኢትዮጵያ ውስጥ የሚመነጭ ውሃ ላይ፣ ቢያንስ ቢያንስ ግማሽ ያህሉን ለመጠቀም አስባችኋል የሚል ውንጀላ ኢትዮጵያ ላይ የሚሰነዘረው ለምንድነው?   
የሐይቁ መጠንና ጥልቀት አልቀነሰም!
የሐይቁ ጥልቀት፣ በ1970 ዓ.ም ከነበረበት ደረጃ፣  በ6 ሜትር ቀንሷል... የሚል መረጃ ልታዩ ትችላላችሁ። ጥልቀቱ፣ በየጊዜው ከፍና ዝቅ እንደሚል ግን፣ ሳይጠቅሱ ያልፉታል። ከ1930ዓ.ም እስከ 1965 ዓ.ም  ከነበረው ጥልቀት ጋር ሲነፃፀር፣ አሁን ያለው የሃይቁ ጥልቀት ይበልጣል(World Lakes Database)።
እንዲያውም፣ ጊቤ1 ግድብ ስራ ከመጀመሩ በፊት ከነበረው ጥልቀትም፣ አሁን ያለው ጥልቀት ይበልጣል። እነዚህ መረጃዎች፣ በሂዩማን ራይትስ ዎች ሪፖርት ውስጥ፣ ሳይጠቀሱ ተዘለዋል።
ይህም ብቻ አይደለም።
ወደ ሐይቁ የሚገባው ውሃ፣ በአብዛኛው (90%) ያህል፣ ከኢትዮጵያ... ማለትም ከኦሞ ወንዝ የሚመጣ ነው ይላል - የሂራዎ ሪፖርት። ይህን ልብ በሉ።
የዩኤንዲፒ ጥናት ደግሞ፣ ቀደም ሲል፣ የኦሞ ወንዝ ድርሻ 80% እንደነበር ይጠቅሳል። ድሮ ድሮ፣ ወደ ሐይቁ የሚገባው ውሃ፣ 80% ከኦሞ ወንዝ፣ 20% ደግሞ እዚያው ኬንያ ከሚገኙ ወንዞች (በተለይም ከቱርክዌል ወንዝ) የሚመጣ ነበር።
ታዲያ፣ ምን አዲስ ነገር ተፈጠረ?
 የዛሬ 25 ዓመት፣ ኬንያ ውስጥ ግድብ ተገንብቷል - በቱርክዌል ወንዝ ላይ። ለምን? ኤሌክትሪክ ለማመንጨትና ለመስኖ። በዚህም ምክንያት፣ ከኬንያ ወንዞች ወደ ሐይቁ የሚገባው የውሃ መጠን ቀንሷል።
ይሄ እውነታ፣ በሂራዎ የ103 ገፅ ሪፖርት ውስጥ አንዴም አልተጠቀሰም። ኬንያ ውስጥ ግድብና መስኖ ሲገነባ፣ ምንም ጥያቄ አይነሳበትም። አይወገዝም። ኢትዮጵያ ውስጥ ግድብና መስኖ ከተገነባ ግን፣ ‘ትልቅ የሰብአዊ መብት ረገጣ’ የሚሆነው በምን ምክንያት ነው?
ኢትዮጵያዊያን ወራሪዎች ናቸው?
በኢትዮ ኬንያ ድንበር አካባቢ የሚኖሩ ከብት አርቢዎችን በሚመለከት ጥናት የሚያካሂዱ ሰዎች፣ በየጊዜው ግጭቶችና የከብት ዝርፊያዎች እንደሚፈፀሙ ይገልፃሉ። በጎሳ ተቧድኖ ግጭትና ዝርፊያ መፈፀም፣ የኋላቀርነት ምልክት መሆኑ አያጠራጥርም። መቅረትም አለበት።
የሂዩማን ራይትስ ዎች ሪፖርት ግን፣ ከሌሎች ሪፖርቶች ይለያል። የጅምላ ውንጀላ ላይ ያተኮረ ነው። በቃ... ኬንያ ውስጥ፣ በጎሳ ተቧድኖ ፣ግጭት የሚቆሰቁስና ዝርፊያ የሚፈፅም አንድም ሰው የለም። ሁሌም ተጠቂዎች ናቸው። ሁሌም በጎሳ ተቧድነው ወረራና ዝርፊያ የሚፈፅሙት፣ የኢትዮጵያ ነዋሪዎች ናቸው - በኬንያዊያን ላይ።አንድ የሰብአዊ መብት ተቋም፣ እንዲህ አይነት፣ የጅምላ ውንጀላዎችን በጭፍን ሲያሰራጭ በጣም ያሳዝናል። ለነገሩ፣ ሰብአዊ መብትን ትቶ፣ “የአካባቢ ጥበቃ”ን ማንገብ የጀመረ ተቋም፣ ውሎ አድሮ ወደ ጭፍንነት መግባቱ እንዴት ይቀርለታል? “የባህል ጥበቃ ተቆርቋሪ” በሚል ሽፋን፣ “በጎሳ የተቧደነ ጥንታዊ የድህነት አኗኗር” ለዘላለም እንዲቀጥል ዘመቻ ማካሄዱም አይገርምም።
እንዴት?
“ሁሉም አካባቢ፣ የሰው እጅ ሳያርፍበት፣ የቀድሞ ገፅታው ‘ተጠብቆ’፣ ለዘላለም መቀጠል አለበት”... የሚል የአካባቢ ጥበቃ ዘመቻ፣ ማንኛውንም ግንባታ፣ በመስኖ እርሻም ይሁን በኢንዱስትሪ መስክ፣ ማንኛውንም የኢኮኖሚ እድገት መቃወሙ የማይቀር ነው። የሂራዎ ሪፖርት፣ ከዳር እስከ ዳር፣ በዚህ የጥፋት ዘመቻ የተቃኘ ነው።
እስቲ አስቡት። ከድህነት መላቀቅና ወደ ብልፅግና መራመድ፣... የተቃውሞ ዘመቻ ሊካሄድበት ቀርቶ፣ ከነጭራሹ ጥያቄ ውስጥ መግባት የሌለበት ጉዳይ መሆን ነበረበት። ትልቁ ችግራችን፣ ከድህነት አለመላቀቃችን አይደለም እንዴ? የመስኖ እርሻ እና የፋብሪካ ስራ አለመስፋፋቱ አይደለም እንዴ? በዘመናዊ እርሻና በኢንዱስትሪ ዘርፍ፣ ኢንቨስትመንት በፍጥነት አለማደጉ አይደለም የቸገረን?
አዎ፤ በኦሞ ወንዝ የሚገነቡ የጊቤ ግድቦች፣ በተለይ ደግሞ፣ የስኳር ፋብሪካዎችና የመስኖ እርሻዎች... በመንግስት ስር ከሚሆኑ ይልቅ፣ በግል ኢንቨስትመንት ቢከናወኑ ኖሮ፣ የብክነትና የመጓተት ኪሳራዎችን ለመቀነስ፣ እንዲሁም ይበልጥ ውጤታማና ጠቃሚ ለመሆን በተቻለ ነበር። ነገር ግን፣ ሂራዎ፣ የግል ኢንቨስትመንትን ይበልጥ ይቃወማል - በጅምላ ‘የመሬት ወረራ’ በማለት ያወግዛል።
ሂራዎ፣ “የኢትዮጵያ የኢንዱስትሪና የመስኖ እርሻ እድገት፣ ለቱርካና ሐይቅ አደጋ ነው” በማለት አለማቀፍ ዘመቻውን የጀመረው ሌላ ጊዜ ቢሆን ኖሮ፣ መራራነቱ ብዙም ላይሰማን ይችል ይሆናል።
 ዛሬ፣ በዝናብ እጥረት ምክንያት ከ8 ሚሊዮን በላይ ኢትዮጵያዊያን የምግብ ተመፅዋች በሆኑበት፣ ከወትሮው የከፋ አመት ላይ፣ ለዚያውም በሚቀጥሉት ወራት፣ እስከ መጪው ክረምት የተረጂዎቹ ቁጥር 15 ሚሊዮን እንዳይደርስ በተሰጋበት አስጨናቂ ዓመት ላይ፣ ግድብንና የመስኖ እርሻን፣ እንዲሁም ኤሌክትሪክንና ኢንዱስትሪን በጭፍን የሚያወግዝ ሪፖርት ማዘጋጀት፣ በጣም መራራ ነው።       

• 34ኛው የቤተ ክርስቲያኒቱ አጠቃላይ የሰበካ ጉባኤ ስብሰባ ሰኞ ይጀመራል

    የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን የአስተዳደር ማዕከል የሆነው የመንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ቤተ ክህነት ጽ/ቤት፣ የሁለትዮሽ የሒሳብ አመዘጋገብ ሥርዐትን በመከተል አሠራሩን ዘመናዊ ማድረጉ ተገለጸ፡፡ ቤተ ክርስቲያኒቱ፣ ዘመናዊውን የሁለትዮሽ የሒሳብ አሠራር /Double entry accounting system/ እንድትከተል፤ የጠቅላይ ቤተ ክህነቱ ጽ/ቤት በባለሞያዎች ያካሔደውን የፋይናንስ ፖሊሲና ማኑዋል ጥናት በቋሚ ሲኖዶስ በማስወሰን ባሳለፍነው የበጀት ዓመት ተግባራዊ ማድረግ መጀመሩ ታውቋል፡፡ በዚህም “ቤተ ክርስቲያኒቱ ዘወትር ስትወቀስበትና ስትተችበት የነበረውን፣ ለቁጥጥር የማያመቸውንና በሕግም ተቀባይነት የሌለውን የነጠላ ሒሳብ አሠራር” ጽ/ቤቱ ማስቀረቱ ተገልጧል፡፡በፖሊሲው ላይ የተመሠረቱና ከማኑዋሉ ጋር የሚስማሙ የሒሳብ ሰነዶችና ቅጻቅጾች ተዘጋጅተው ጥቅም ላይ የዋሉ ሲሆን የጽ/ቤቱ የሒሳብና በጀት መመሪያ ሠራተኞችም ለትግበራው የሚያስፈልጉ ልዩ ልዩ ሥልጠናዎችን እንዲያገኙ ተደርጓል፡፡
የተቋሙን አጠቃላይ ሀብትና ዕዳ በማወቅ፣ የፋይናንስና የንብረት አጠቃላይ አስተዳደሩንና እንቅስቃሴውን ለቁጥጥር ግልጽ ለማድረግ፤ ተፈላጊውን መረጃ በሪፖርት በማውጣትና በመተንተን ተገቢ ውሳኔ ለመስጠት ምቹ የሆነውን የሁለትዮሽ አመዘጋገብ ተግባራዊነት ተከትሎ፣ ጽ/ቤቱ ማዕከላዊ የሒሳብ አሠራር በመከተሉ፣ ወጪ ቆጣቢና ውጤታማ ሥራ ለማከናወን መቻሉ ተገልጧል፡፡ ከ16 የጽ/ቤቱ መመሪያዎችና ድርጅቶች፣ በጀታቸውን በራሳቸው እያንቀሳቀሱ ሲሠሩ የነበሩት የሰባቱ የገቢና ወጪ ሒሳብ በአንድ ቋት ተጠቃልሎ በሁለትዮሽ አመዘጋገብ ዘዴ በመሠራቱ ከሐምሌ 1 ቀን 2006 ዓ.ም. እስከ ጥቅምት 30 ቀን 2007 ዓ.ም. ድረስ የተሠራው ሒሳብ ተመርምሮ ተዘግቷል፡፡ ቤተ ክርስቲያኒቱ በየጊዜው በሚታየው የዋጋ ግሽበት ተጎጂ ሆና የቆየች ሲሆን በሕጋዊና አስተማማኝ የግዢ ሥርዐት ዓመታዊ ግዥ በመፈጸም ዕቃዎች በመጋዘን እንዲቀመጡ በማድረግ፣ ከጉዳቱ ለመዳን መቻሉ በመረጃው ተጠቅሷል፡፡ የጠቅላይ ቤተ ክህነቱ ሠራተኞች የደመወዝ ክፍያ፣ የቤቶችና ሕንፃዎች ኪራይ አሰባሰብ በባንክ በኩል በማስፈጸም ሒደቱን ቀልጣፋ በማድረግ ውጤታማ ሥራ መሠራቱ ተመልክቷል፡፡
በአሁኑ ወቅት በአገር ውስጥና በውጭ ለተቋቋሙት 50 አህጉረ ስብከት የበላይ ሓላፊና አመራር ሰጪ የሆነው የጠቅላይ ቤተ ክህነት ጽ/ቤት ዋነኛ የፋይናንስ ምንጭ፣ ቤተ ክርስቲያኒቷ በየአጥቢያው ባቋቋመቻቸው ሰበካ ጉባኤያት የሚሰበሰበው የገንዘብ አስተዋፅኦ ነው፡፡ ከ34 ዓመታት በፊት በሳንቲም ደረጃ የተጀመረውና ለጽ/ቤቱ ፈሰስ የተደረገው የሰበካ ጉባኤያት ጠቅላላ ገቢ በበጀት ዓመቱ ከብር 125 ሚሊዮን በላይ መድረሱ የተገለጸ ሲሆን ይህም ካለፈው ዓመት ከ30 ሚሊዮን ብር በላይ ብልጫ እንዳለው ተመዝግቧል፡፡
የገቢዋ ዕድገት ቤተ ክርስቲያኒቷ መንፈሳዊ፣ ማኅበራዊና ልማታዊ አገልግሎቶቿን በራስዋ አቅም ለማከናወን እንደሚያስችላት የሚታመን ሲሆን ለዚህም ጠቅላይ ጽ/ቤቱ መከተል የጀመረው ዘመናዊው የሁለትዮሽ የሒሳብ አያያዝ በተዋረድ በሁሉም አህጉረስብከት እና አጥቢያ አብያተ ክርስቲያናት ተግባራዊ እንዲሆን ተጠይቋል፡፡ በቀጣዩ ሰኞ በጽ/ቤቱ አዳራሽ የሚጀመረውና ከ800 ያላነሱ የመላው አህጉረ ስብከት ልኡካን የሚሳተፉበት 34ኛው አጠቃላይ የሰበካ መንፈሳዊ ጉባኤ ዓመታዊ ስብሰባ በጉዳዩ ላይ ጠንካራ የጋራ አቋምና ውሳኔ እንደሚያሳልፍ ይጠበቃል፡፡

በጎጃም በርካታ ሰዎች እንዲረሸኑና በጅምላ እንዲቀበሩ አድርገዋል ተብሏል


በደርግ የአገዛዝ ዘመን ዜጎችን በመግደል፣ በማሰርና በማሰቃየት ተከስሰው ሞት የተፈረደባቸው አንድ ስማቸው ያልተገለጸ የቀድሞ የደርግ ባለስልጣን፤ በሆላንዷ ከተማ አምስቴልቪን በፖሊስ ቁጥጥር ስር መዋላቸውን ኤንኤል ታይምስ የተባለው የአገሪቱ ድረገጽ ትናንት ዘገበ፡፡
በሆላንድ የሚገኘው የአለማቀፍ ወንጀሎች ምርመራ ቡድን አቃቤ ህግ፣ ግለሰቡ እ.ኤ.አ በ1978 ባስተላለፉት ትዕዛዝ፣ በጎጃም አካባቢ ታስረው የነበሩ በርካታ ሰዎች ተረሽነው አስከሬናቸው በጅምላ መቃብር እንዲቀበር ተደርጓል ማለታቸውን ዘገባው ገልጧል፡፡ተጠርጣሪው ከሁለት ሳምንታት በፊት በፖሊስ ቁጥጥር ስር እንደዋሉ የጠቆመው ዘገባው፣ አምስቴልቪን ከተማ ውስጥ በሚገኘው የግለሰቡ መኖሪያ ቤት ውስጥ በተደረገ ፍተሻ የተለያዩ ማስረጃዎች የተገኙ ሲሆን በሄግ የሚገኘው ፍርድ ቤትም ከትናንት በስቲያ በዋለው ችሎት፣ ግለሰቡ ለ90 ቀናት በእስር ላይ እንዲቆዩ ወስኖባቸዋል ብሏል፡፡የሆላንድ ፖሊስ ግለሰቡ የተጠረጠሩባቸውን የወንጀል ድርጊቶች ስለመፈጸማቸው ምርመራ ማድረግ መጀመሩን ዘገባው ገልጾ፣ ፖሊስም የምስክሮችን ቃል መቀበሉንና ተጠርጣሪው ድርጊቶቹን ስለመፈጸማቸው ምስክርነታቸውን ከሰጡ ግለሰቦች አብዛኞቹ በውጭ አገራት የሚኖሩ ኢትዮጵያውያንን  እንደሆኑ አስታውቋል፡፡ምስክሮቹ በሰጡት ቃል ግለሰቡ በጎጃም አካባቢ የደርግ ባለስልጣን ሆነው ባገለገሉባቸው አመታት የተጠቀሱትን የወንጀል ድርጊቶች ስለመፈጸማቸው ተናግረዋል ያለው ዘገባው፣ የሆላንድ የወንጀል ምርመራ ባለስልጣናትም ግለሰቡን ለሞት ቅጣት ያበቃቸውን የወንጀል ክስ የተወሰነ መረጃ ከኢትዮጵያ መንግስት ባለስልጣናት መረከቡን ገልጧል፡፡የአለማቀፍ ወንጀሎች ምርመራ ቡድን፣ በደርግ የአገዛዝ ዘመን በደብረ ማርቆስና በመተከል እስር ቤቶች ውስጥ የግድያና የስቃይ ድርጊቶችን በፈጸሙ ግለሰቦች ላይ ትኩረት በማድረግ ምርመራ እያደረገ እንደሚገኝ ዘገባው አስታውቋል፡፡
61 አመታቸው እንደሆነ የተነገረላቸው እኒሁ ባለስልጣን፤ ከጥቂት አመታት ወዲህ ነዋሪነታቸውን በሆላንድ እንዳደረጉና የአገሪቱ ዜግነት እንደተሰጣቸው ያስታወሰው ዘገባው፣ ግለሰቡ በኢትዮጵያ ፍርድ ቤት በሌሉበት የእድሜ ልክ እስራትና የሞት ቅጣቶች እንደተጣሉባቸውም ገልጧል፡፡



 ታዋቂው የኮምፒውተርና የስማርት ፎን አምራች ኩባንያ አፕል በዊስኮንሲን ማዲሰን ዩኒቨርሲቲ ስም የተመዘገበን የፈጠራ ውጤት በሚያመርታቸው አይፎን 5 ኤስ፣ አይፎን 6 እና አይፎን  6 ፕላስ ሞባይሎቹ ውስጥ ተጠቅሞ በመገኘቱ እስከ 862 ሚሊዮን ዶላር የሚደርስ ቅጣት ሊጣልበት እንደሚችል ተዘገበ፡፡ፕል ይህንን በዩኒቨርሲቲው ባለቤትነት ስር የሚገኝ የተለየ አይነት ፕሮሰሰር ከሞባይሎቹ በተጨማሪ በአንዳንድ የአይፖድ ምርቶቹ ውጥስ መጠቀሙን የጠቆመው የኢንዲፔንደንት ዘገባ፣ ኩባንያው ግን የዩኒቨርሲቲው የባለቤትነት መብት ውድቅ የተደረገ በመሆኑ ልወነጀል አይገባም ሲል ተከራክሯል፡፡
ጉዳዩን ሲመለከት የቆየው የማዲስን ፍርድ ቤት ግን ቴክኖሎጂውን የተጠቀምከው ባለቤቱን ሳታስፈቅድ ነው ሲል አፕልን ጥፋተኛ እንዳደረገውና ዊሊያም ኮንሊ የተባሉ ዳኛም አፕል በካሳ መልክ እስከ 862 ሚሊዮን ዶላር እንዲከፍል ሊፈረድበት እንደሚችል መናገራቸውን ዘገባው ገልጧል፡፡

  - አማጺው የሰላም ስምምነቱን አፍርሼ ወደ ጦርነት እመለሳለሁ ብሏል
                 
    የደቡብ ሱዳን ፕሬዚዳንት ሳልቫ ኬር የአገሪቱ ግዛቶች ቁጥር ከ10 ወደ 28 ማደግ አለበት ሲሉ ያስተላለፉት አወዛጋቢ ውሳኔ፣ ባለፈው ማክሰኞ ልዩ ስብስባውን ባከናወነው የአገሪቱ የሚኒስትሮች ምክር ቤት ተቀባይነት ማግኘቱን ቢቢሲ ዘገበ፡፡
የፕሬዚዳንት ሳልቫ ኬር የግዛት ቁጥር ጭማሬ እርምጃ፣ ከአለማቀፉ ማህበረሰብ በስፋት ተቃውሞ ሲገጥመው እንደነበር ያስታወሰው ዘገባው፣ ኢጋድም የፕሪዚዳንቱ ውሳኔ በምክር ቤቱ ተቀባይነት ማግኘቱ በአገሪቱ ተቀናቃኝ ሃይሎች መካከል የተፈረመውን የሰላም ስምምነት የሚጻረር ነው ሲል እንደተቸው ገልጧል፡፡
ውሳኔው ተግባራዊ የሚሆነው የደቡብ ሱዳን ፓርላማ ካጸደቀው በኋላ እንደሚሆን የጠቆመው ዘገባው፣ አንዳንድ የአማጺው ሃይል አባላትም ውሳኔው የማይሻር ከሆነ የሰላም ስምምነቱን አፍርሰው ዳግም ወደ ትጥቅ ትግል እንደሚገቡ ማስጠንቀቃቸውን ገልጧል፡፡
የአማጺው ሃይል አመራሮች የፕሬዚዳንት ሳልቫ ኬርን ውሳኔ ህገ መንግስታዊ ያልሆነና ባለፈው ነሃሴ ወር በሁለቱ ሃይሎች መካከል ከተፈረመው የሰላም ስምምነት ያፈነገጠ ነው ሲሉ መተቸታቸውን የዘገበው ደግሞ ሱዳን ትሪቢዩን ነው፡፡ፕሬዚዳንት ሳልቫ ኬር ከሁለት ሳምንታት በፊት በአገሪቱ የቴሌቪዥን ጣቢያ በኩል የአገሪቱን ግዛቶች ቁጥር ለማሳደግ መወሰናቸውን ይፋ ማድረጋቸውን ያስታወሰው ዘገባው፣ በወቅቱም ይህን ያልተጠበቀ ውሳኔ ያስተላለፉት ለደቡብ ሱዳን ህዝቦች ጥያቄ ምላሽ ለመስጠት እንደሆነ ማስታወቃቸውን ገልጧል፡፡
ፕሬዚዳንት ሳልቫ ኬር ደቡብ ሱዳን 10 ግዛቶች ያሏት አገር ናት የሚለውን የህገ መንግስቱ አንቀጽ 162 እንዲያሻሽሉ ለአገሪቱ ህግ አርቃቂዎች ጥሪ ማስተላለፋቸውንም ዘገባው አስታውሷል፡፡