Administrator

Administrator

Tuesday, 04 March 2014 11:21

የገንዘብ ቀለማት!

“ገንዘብ ንጉሥም ሎሌም ያደርግሃል”

ሲጀመር
የልጆች የአስተሳሰብ  ነፃነት መቼም ያስቀናል። እኛ ትልልቆቹ በማህበራዊ፣ ሀይማኖታዊ፣ ዘልማዳዊ ፣ መንግስታዊ ፣ ምናምናዊ--- ወጥመዶች አስተሳሰባችንን ከማሰራችን በፊት ያለውን ንፅህና ማለቴ ነው፡፡ ይህንኑ ባርነታችንን እንደሚረባ ውርስ፣ ሲለን በሽንገላ ሳይለን በቁጣ፣ አሳልፈን ነፃነታቸውን እስክንነጥቃቸው ያለውን፡፡ የነፃነታቸው መገለጫ ደሞ ያልተገደበው ንግግራቸው ይመስለኛል፡፡ ድንገት ሲያወርዱት፣ ለእኛ ለትልልቆቹ፣ በባርነት ላለነው የአይምሮ ፈተናም የሃሳብ ፍንዳታም ነው፡፡
 አንድ ማታ እቤት እራት እየበላን ነበር።  ናታን፣ እድሜ 9፣ በትንንሽ እጆቹ የእንጀራ ቁርጥራጮች እያንገላታ “ሀብታም ብንሆን ደስ ይለኝ ነበር” አለ። ለተወሰኑ ደቂቃዎች ፀጥታ ሆነ፡፡ ሃሳብ ፈነዳ። በቀላሉ “እኔም ደስ ይለኝ ነበር” ብሎ ለመዝጋት የወላጅነት ህሊና ይፈቅድ እንደሆን እንጃ፡፡ በተቃራኒው “ገንዘብ አጋንንታዊ ነው፡፡ ባለህ መደሰት አለብህ ምናምን” ብሎም ለማለፍ፣ ለወላጅ ግልግል  ቢመስልም ፣ ህፃኑ ይቀበለዋል ወይ ብሎ ማሰብ የአባት ነው፡፡ ከእኛው ጀምሮ፣ በትምህርት ቤትም በመዝናኛም በመፅሃፍትም፣ ሁሉ ቦታ  ሰበካው ሁሉ  ገንዘብና ሀብት ነው፡፡ ለወላጅ “ገንዘብ የለኝም” ፣ “ገንዘብ ሳገኝ---” እና የመሳሰሉት ለሕፃናት የሚሰጡ የዘወትር  መልሶች ናቸው፡፡ እናማ “ባለፈው ሎተሪ ከደረሰን ዱባይ እንሄዳለን ተብያለሁ” ብሎ ቀን ሲቆጥር የነበረ ህፃን፣ ሀብታም መሆንን ቢመኝ ምኑ ይገርማል? እኔ ግን  መጠየቄ አልቀረም -
“ምን ማለት ነው ሀብታም መሆን?”
“ብዙ ብር ማግኘት”
“ምን ለማድረግ?”
“ቲቪ ለመግዛት! እነ እንትና እኮ ሀብታም ናቸው። እሱ ክፍል  ቲቪ አለው፡፡ እኔም ቲቪ እፈልጋለሁ” አለኝ ናታን፣ የአንዱን ጓደኛውን ስም እየጠራ፡፡
የተንተባተበ ነገር መልሼለት ፣ ነው ሰብኬው፣ ባለህ ብትደሰትስ ምናምን  ብዬው አለፍኩት። “ሴክስ” ምንድነው ብሎ እንዳፋጠጠኝ ቀን፣ የራሴው ቃላት ከጉሮሮዬ ተቀርቅረውብኝ፣ የፈለኩትን ሳይሆን የተባልኩትን አሳልፌ ሰጥቼው፣ የወሬውን ቻናል አስቀይሬ አረሳሳሁት፡፡
ይቆጠቁጠኝ ገባና ፣ ማሰቤን ቀጠልኩ፡፡ እንዲህ ብለውስ ኖሮ አልኩኝ…..
….የገንዘብ ሀይል ምትሃታዊ  እንጂ ጋኔላዊ አይደለም። ገንዘብ በራሱ ያሰክራል እንጂ ነፍስ አያረክስም፡፡  ገንዘብ ነፃነትንም ባርነትም አጣምሮ የያዘ ይመስለኛል፡፡ ይህን ሀይል በቅጡ መረዳት ከፈለግህ  መልሱ ያለው እውስጥህ እንጂ ከውጭ አይደለም፡፡ ገንዘብን ቀርበህም እርቀህም ማየት፣ ያየኸውንም ከውስጥህ ማስታረቅ ግድ ይልህ ይሆናል፡፡ እኔ ግን የገባኝን ልንገርህና መነሻ ከሆነህ ጥሩ፣ ከረከሰብህና የተሻለ የመሰለህን ካፈለቅህም እሰየው። ልጅ ከወላጆቹ የተሻለ ካላሰበ ፣ ወላጆች የተፈጥሮን ግዴታ ከማሟላት ያለፈ ስራ አልሰሩም ማለት አይደል?
ይኸውልህ እንግዲህ….ገንዘብ  ቁሳዊ፣  ማህበራዊና ስነልቦናዊ  ገፅታዎችን ያዘለ ነው፤  እየረቀቁ የሚሄዱ የተሳሰሩ ትርጉሞችን ያቀፈ አስገራሚ የሰው ልጅ ፈጠራ። አዎ እንደምትመገብበት ሳህን ሰው ሰራሽ ቢሆንም፣ የሰው ልጅ ሊገለገልባቸው ሰርቶ ተገልብጠው ጌታው ከሆኑበት ውልዶቹ ገንዘብ ምናልባትም ቀዳሚው ነው፡፡
ቁሳዊው ሀይሉ የሚመነጨው ገንዘብ ባንተና በምትፈልጋቸው ወይም ያስፈልጉኛል ብለህ በምታስባቸው ነገሮች መሃል ርቀትን መፍጠር በመቻሉ ነው፡፡ ገንዘብ ባልነበረበት ዘመን እንዴት ነበር ብለህ እስኪ አስብ፡፡ የሚያስፈልግህን አድነህ፣ ካልሆነ ቆፍረህ ሲልም ሁለት ሶስቱን አንድ ላይ አስረህ ትገለገላለህ። ተፈጥሮ ታቀርብልሃለች፣ አንተ ታመሰግናታለህ። ጅል ካልሆንክ በስተቀር ለማያስፈልግህ ጉልበትህን አታባክንም፡፡ የሚያስፈልግህን ውስጥህ ይነግርሃልና ሌሎች እንዲወስኑልህ አትጠብቅም፣ ምናልባትም አትፈቅድም፡፡
አሁን ነገሮች እንደዛን ዘመን ቀላል አይደሉም። ሲጀምር የሚያስፈልጉህ ነገሮች ምግብና ከወገብ በታች የምታገለድመው ብጣሽ ቅጠል አይደለም።  በቃኝ ማለት ብትችል እንኳ፣ እራስህን ከዋሻ ቆልፈህ ካልዘጋህ በስተቀር የምትኖርበት ህብረተሰብ፣ እኔንም ጨምሮ፣ አበድክ ብለን ሰው ሰራሽ ዋሻ ውስጥ እንቆልፍሃለን፡፡
ስለዚህ  በእኛ መለኪያ፣ እንደ ጤነኛ ሰው የሚያስፈልግህን ካበዛኸው ገንዘብ ማግኘት ግድ ይልሃል፡፡ በምትፈልጋቸው ነገሮችና በማግኘትህ መሃል ገንዘብ መሰናክል ሆኖ ቆሟል ማለት ነው። ምን ያህል ገንዘብ የሚለው ትርጉም አልባ ነው፡፡ ሁሌም የፍላጎትህ ደንቃራ ገንዘብ ሆኖ ታገኘዋለህ። ምንም ያህል ወደምትፈልገው ብትጠጋ፣ ምንም ያህል የገንዘብ እጦት የዘጋብህን በሮች ብትከፍት፣ የጎደለህን እስክትሞላ የምትፈልገው ከፍላጎትነት ሳያልፍ ይቆይሃል፡፡ አገኘሁት ስትል የሚርቅህም ብዙ ነው፡፡      
ሁሉንም ባትችልም ታዲያ ፣ የምትፈልጋቸውን ነገሮች በሂደት ማግኘትህ አይቀርም፡፡ አንዳንዱን በቀላል፣ ሌላውን ለፍተህ የግልህ ታደርጋለህ። ደሞ ያኛው ዋጋ የማይወጣለትን ያሰዋሃል፡፡ ካገኘሃቸውም በኋላ ፣ አንዳንዱ የምትጠቀምበት፣ ሌላው ቢቀር ምንም የማያጎድልብህ ሆኖ ሊሰማህ ይችላል፡፡ ያኛው ደሞ በጊዜያዊ ሞኝነት ተታለህ  እንጂ እድሉ ቢሰጥህ ደግመህ የማትሰራው ስህተት መስሎ ይታይህ ይሆናል፡፡
ግን ሁለት ነገሮች አይቀሬ ናቸው፡፡ አንድም ያ እንደዛ የለፋህለት፣ ተሟላ ብለህ የተደሰትክበት ፍላጎትህ ክብሩን ያጣብሃል፡፡ ያንተ ያልነበረው ያንተ ሲሆን፣ በሌሎች እጅ ያማረህ ተራ ይሆንብሃል፡፡ ዋጋ ከፍለህ ገንዘብ ሰርተህ፣ ቁሳቁስ ገዝተህ ያገኘህ የመሰለህ ልባዊ እርካታ፣ እንደ በልግ ዳመና ድንገት ብን ብሎ ይሰወርብሃል፡፡ ገንዘብ ጊዜያዊ ደስታ ሰጥቶህ መልሶ ይነጥቅሃል፡፡
ያን ጊዜ፣ በሁለተኛ ደረጃ፣ ካለህ የተሻለ ፍለጋ ታንጋጥጣለህ፡፡ የሚገርምህ ታዲያ ካንተ የተሻለ ያላቸው ብዙሃን እንደሆኑ ትረዳና፣ አዲስ ፍላጎት ፈጥረህ፣ ያለህን ንቀህ በምትፈልገውና በአንተ መሃል እንደገና ገንዘብን ደንቃራ ትገትራለህ፡፡ እንዳንተው፣ አንተ ባለህ ማልለው፣ እነሱ ሽቅብ አንተ ቁልቁል የምታያቸውም ብዙሃን እንደሆኑም አትገነዘብም፡፡ ወደ ላይ አንገትህን ሰብረህ እንዴት ወደ ታች ልታይ ትችላለህ? የገንዘብ የመጀመሪያው ምትሃታዊ ሀይሉ እዚህ ላይ ነው፡፡
እንዳትሳሳት አደራህን! 1 ሺህ ወይም 1 ቢሊዮን አልያም ከዛም በላይ ይኑርህ፣ አይኑርህ እያልኩህ አይደለም፡፡ ግን ምንም ያህል ገንዘብ እንደ ፈንዲሻ በድስትህ ሲንከተከት ቢውል፣ ምትሃታዊ ሀይሉ ካወረህ ቅምም አይልህም  ማለቴ ነው፡፡
ይህንን አልፈህ ማየት ስትችል - ከፍ ስትል ማለት አይደል? - የገንዘብ  ማህበራዊ ትርጉም ሌላ ፈተና አዝሎ ያፈጥብሃል፡፡

ሲቀጥል----
ባጭሩ ሁለት ነገር ላስጨብጥህ ሞክሬያለሁ። ገንዘብ በራሱ ጥፋተኛ እንዳልሆነ፣ ሆኖም የፍላጎታችን ጣሪያ አድማሳዊ ብቻ ስለሆነ፣ የሚበቃንን ያህል መቼም ማግኘት እንደማንችል ነገርኩህ፡፡ ይህም ለገንዘብ ያልታቀደለትን ሀይል እንዳጎናፀፈውም አወራን፡፡
ይህንን ተከትሎ ሁለተኛው የገንዘብ ምትሃት ያለው ከማህበራዊ ገፅታው ላይ ይመስለኛል፡፡ ያለህ የገንዘብ መጠን በምትኖርበት ማህበረሰብም ሆነ ከዛ በዘለለ ከባለፀጎች ተርታ  ያስመድብሃል፡፡ ከመናጢ ድሃ ይጀምርና፣ መካከለኛ ደሃ፣ ከድህነት ሊወጣ የደረሰ፣ መሃል ሰፋሪ፣ ጀማሪ ሀብታም፣ የናጠጠ ሀብታም ሌላም ሌላም እየተባለ ማህበረሰቡ ይከፋፈላል፡፡  እያንዳንዱ ክፍል ከታቹ ካለው የበለጠ፣ ከላይ ካለው ያነሰ “ሀይል/ጉልበት” አለው፡፡ ይህ ጉልበት የገንዘብ ማህበራዊ ምትሃት መቀመጫ ነው፡፡
ጉልበቱ ምንድ ነው አትልም?
ነገሮችን ከመግዛት አቅም ተከትሎ የሚመጣው ሰዎች ባለህ ሀብት መጠን የሚሰጡህ ቦታና ክብር ነው። በዚያው ምልከታ የምትገዛቸው ነገሮች መጠቀሚያ ብቻ ሳይሆኑ ያለህበትን የማህበረሰብ ክፍል መግለጫም ናቸው፡፡ ይህን ያህል ገንዘብ አለኝ፣ ሀብቴ ይህን ያህል ነው፣ እንደዚህ ብላችሁ ልታዩኝ ይገባል፣ በናንተ መሃል ያለኝ ደረጃ ይኸውላችሁ ---- ብለህ የምታውጀው በምትገዛቸው ቀሳቁሶች ዋጋ ሸፍነህ ይሆናል፡፡ ያኔ ከአንተ በታች ያሉትን ቁልቁል የማየትን ሀይል ገንዘብ ይሰጥሃል፡፡ እነሱም ባለህ ሀብት ያከብሩሃል፡፡ ድሮ ቢሆን  የሀገር ንጉስም ሊያደርግህ ይችል ነበር፡፡ አሁንም ትንንሽ ንግስናዎች ያንተ ይሆናሉ፡፡ ከዚህም የአሸናፊነትን፣ የስኬትን መንፈስ ታጭዳለህ፡፡ ያሰክርሃል ቢባል ያስኬዳል፡፡
የሀብት ደረጃዎችን  ስትቀበል፣ የስኬትህ  መለኪያነታቸውንም ያንተ ማድረግህ ግድ ነው፡፡  መቶ ብር ካረረበት ጀምሮ፣ ቢሊየነር እስከምትለው፣ ሁሉም ያለውን ምድራዊ ስኬት ባለበት የሀብት ክፍል ለመለካት ሲገደድ፣ ገንዘብ የቁሳዊ ፍላጎት ማሟያ መሆኑን አልፎ መጠሪያ ይሆናል፡፡ ለዚህም ነው በየጊዜው የአገራችን 100 ሁብታሞች፣ የአለም አንደኛ ሀብታም፣ የአፍሪካ ደሃዋ አገር እየተባለ ደረጃ የሚወጣው፡፡ በግልባጩ ከተመደብክበት የሀብት ደረጃ  በላይ ያሉትን መመልከትህ አይቀርም፡፡ “የት ጋ ነው ያለሁት?” ብለህ ትጠይቃለህ፣ ከበላይህ ብዙ ደረጃዎች  ይታዩሃል።  ከፍ ወዳለው ክፍል መግባትን ትሻለህ፤ የንግስና ርስትህን ለማስፋት መሆኑ ነው፡፡
ገንዘብ መጠሪያህ ከሆነ በኋላ ማብቂያ የለውም። ሁሌም ብዙ ገንዘብ ስምህን ተከትሎ እንዲጠራልህ ትፈልጋለህ፡፡ የቱንም ያህል ብታባክነው የማያልቅ ገንዘብ ብትይዝ፣ በሀብት ምድብ ቁንጮ ላይ  ብትቀመጥ፣ በስምህ የተመዘገበልህን ለመጨመር ስትል ብቻ ገንዘብን ትሻለህ፡፡ ይህን ጊዜ ገንዘብ ሁለተኛውን ምትሃቱን ጣለብህ ማለት ነው፡፡ ከሰዎች በልጦ መታየትን አቅምሶህ፣ የዘላለም ሱሰኛው አደረገህ፡፡
ገንዘብ ንጉስም ሎሌም አደረገህ ማለት አይደል፡፡

መጨረሻው
ገንዘብን ለጥቅሙ ሳይሆን ለስሙ ስትል ማሳደድ ከጀመርክ፣ ያንተው የስነልቦናህ አካል ይሆንልሃል፡፡ ይህንን ሲያደርግ ጫማ ቆንጥጦ ሽቅብ እንደሚያዘግም ጉንዳን፣ ሳታየው በዝግታ ነውና የማንነትህ አካል፣ የስሪትህ ምሰሶ ሲሆን ላታውቀው ትችላለህ፡፡ ያለህ ገንዘብ የስራህን ስኬት መግለፅ ብቻ እጣው ሊሆን ሲገባ፣ የልብህ ማማ እንዲሆን ስትፈቅድለት ፣ እሱ ጌታ አንተን ሎሌ የማድረግ ስልጣንን ይቀዳጃል፡፡ ሶስተኛው ምትሃትም እዚህ ላይ ነው ያለው፤ ገንዘብ ከላይ ያወጋናቸውን ውጫዊ ገፅታዎቹን ዘሎ ነፍስህ ላይ ሲጠመጠም የማይነካ ኃያል ይሆንብሃል፡፡  
ምትሃቱን የሚያገኘውም በሁለት ምክንያት ይመስለኛል፡፡
መጀመሪያ ገንዘብን በዚህ መልኩ ስታሳድደው፣ ለክብሩ ብለህ የምትፈፅማቸው ድርጊቶች በአብዛኛው ንፁህም  ህጋዊም አይሆኑም፡፡ ሱሰኛ ነህና እሱን ለማርካት ስትል አስተካክለህ ከተከልከው ከማጨድ ይልቅ ካልዘራህበት መሻትህ ግድ ነው። በስራ ብቻ ካለህበት ፈቀቅ ማለት ሲከብድህ፣ የምታልመውን የተሸነቆረ የገንዘብ ጎተራ በስራህ ልትሞላው እንደማትችል ስትረዳ፣ ሌሎች ሰርቀው ሲከብሩ፣ ከታችኛው ምድብ በድንገት ተፈትልከው ከላይኛው ሲሰኩ፣ የምትኖርበት ህብረተሰብ ተሸናፊ ነህ ብሎ ሲሳለቅብህ ፣ አንተም ሽንፈት ይውጥሃል፡፡ ስለዚህ ላለመሸነፍ ስትል አንተም ትገባበታለህ፡፡ ሲሰርቁ ትሰርቃለህ፡፡ ተራ ሌባም ባትሆን፣ ያንተ ባልሆነው መክበርን መሻትህ  ግን ከተራዎቹ ተርታ ያስመድብሃል፡፡
ሰርቀው ላልተያዙ ሲጨበጨብ አብረህ ታጨበጭባለህ፡፡ መስረቅን ሸሽተው ከድሃው ተርታ በተመደቡ ሲሳለቁ፣ በስንፍናቸው ሲገረሙ ትታደማቸዋለህ፡፡ ‹‹ሲሾም ያልበላ ሲሻር ይቆጨዋል›› የእለት ፀሎትህ አካል ይሆናል። ለገንዘብ ብለህ ዋጋ የማይወጣላቸውን ነገሮች ስታጣ ብዙም አይሰማህም። ከጓደኛህ ነጥቀህ ስትከብር ትደሰታለህ፣ ብዙዎችም በተራህ ያጨበጭቡልሃል፡፡ የቤተሰብህን ፍቅር በገንዘብ ስትለካ ምንም አይመስልህም፡፡
ታሪክ መሰረት ከሆነን ደሞ፣ እያንዳንዱ ስርቆት ቅጣትን ሳይሆን ሽልማትን ሲያድል ታያለህ። መጀመሪያ ግራ ይገባህ ይሆናል፣ ከዛ መቀበልን ትመርጣለህ፣ በመጨረሻም መብትህ እንደሆነ ትቆጥረዋለህ፡፡ ከሽልማቱም አልፎ የስርቆትን ድብብቆሽ ትወደውም ይሆናል፡፡  መጀመሪያ በፍራቻ ታጥረህ የፈፀምከው ስርቆት ልምድህ ሲዳብር እንደ ጥሩ ጨዋታ ማየትም ትጀምራለህ፡፡ በደም ስሮችህ የሚለቅብህን እፅ አጣጥመህ ትወደዋለህ ቢባል ማጋነን አይሆነም፡፡  
በሁለተኛ ደረጃ በእጅህ ያለህን የማጣት ፍርሃት ይጠናወትሃል፡፡ ልብ በል! ምንም የሚያስፈራህ ነገር እንኳን ባይኖር ፣ ቀናቶች የሚሰግዱልህ ቢመስልህ፣ የማጣት ፍርሃት ግን የቀን ተሌት ህልምህ አካል ይሆናል፡፡ የገንዘብ ማግኘት ሱስህን ከፍ ወዳለው ደረጃ የማሻገር አቅም ያላቸው ነገሮች መሪ ሆኖ እንዲቀመጥ ትፈቅድለታለህ፡፡ ከማጣት ፍርሃት ለመገላገል  መልሱ የበለጠ፣ የማያልቅ ገንዘብ ነው ብለህ ስለምታምን ለዚሁ ትንከራተታለህ፡፡ የማያስፈልግህን ላታገኘው!  
ይሄን ጊዜ ሶስተኛውና የመጨረሻውን ምትሃቱን ገንዘብ አሰፈረብህ ማለት አይደል? ስራውን ጨረሰ! እስከመጨረሻው ጌታህ ሊሆን ዙፋኑን ተቆናጠጠ፡፡
እናማ ምን ይሻላል ካልከኝ ፣ ጥቂት ልጨምር፡-
ቤንጃሚን ፍራንክሊን እንዳለው “ገንዘብ ደስተኛ እድርጎን አያውቅም፣ ሊያደርገንም አይችልም። ገንዘብ በራሱ ደስታን ማምረት የሚያስችለውን ስጦታ አልታደለም፤ ባገኘነው መጠን ጭማሪ እንሻለን እንጂ።” ደስታና እርካታም ይለያያሉ፡፡ ገንዘብ ሁለቱንም ሊሰጥህ የሚችለው አጠቃቀምህን ተከትሎ ነው። በገንዘብ ከምትገዛቸው ነገሮች እርካታን እንጂ ደስታን አትሻ፡፡ እርካታ አንፃራዊ ስለሆነ፣ የተሻለ ቁስ የበለጠ እርካታ ይሰጥሃል፡፡ እርካታ እንዲሁ ጊዜያዊ ነው፡፡ ሁሌም እድሳት ይፈልጋል፡፡
በተመሳሳይ ደስታንም አንፃራዊና ጊዜያዊ አድርገህ መመልከት ግን ስህተት ይሆናል፡፡ ከገንዘብ ደስታን የምትሻ ከሆነ፣ ካለህ ላይ ለሌላቸው ወይም ላነሳቸው ያለቅድመ ሁኔታ አሳልፈህ ስጥ። በማትጠቀምበት ቁሳቁስ መከበብን አትምረጥ። የህይወት ስኬትህን በገንዘብ ሳይሆን ባሉህ ዋጋ የማይወጣላቸው በረከቶች መዝነው፡፡ ይህ ከተሳካልህ ገንዘብ ከመገልገያ መሳሪያነቱ እንደማይዘልብህ እርግጠኛ መሆን ትችላለህ። የገንዘብን መጥፎ ገፅታ እስከገባኝ ነገርኩህ፣ ጥሩውንማ እራሱ ያስተምርህ የለ? …..ብዬ ናታንን ብመክረው ምን ያህል ትርጉም ያገኝበት እንደሆነ አንጃ፡፡ ከዛ አልፎ “ደስታ ግን ምንድነው?” ካለኝ ሌላ አርእስት አገኘን ማለት አይሆንም?

  • የት አገር ነው የፓርቲ ልሳን አባላት ጋዜጠኞች የሚባሉት?
  • እጃችሁን ሰብስቡ ስንል ከሰበሰቡ እሰየው! ካልሰበሰቡ እናጋልጣቸዋለን
  • ‹‹የኢትዮጵያ ጋዜጠኞች መድረክ›› ስለሚባሉት ምንም  መረጃ የለኝም

ባለፈው ማክሰኞ ኢብጋህ፣ ኢነጋማ እና ኢገማ የጋራ መግለጫ መስጠታችሁ ይታወሳል፤ ዓላማው ምንድን ነው?
የተለያዩ ፅንፈኛ አክራሪ ወገኖች፣ የጋዜጠኝነት ሞያን ለእኩይ ተግባራቸውና ለዓላማቸው ማስፈፀምያ ለማዋል ጠይቀውን ነበር፡፡ ይሄንንም ተግባር ለመቀበልና ተባባሪ ሆነን ለመቅረብ ፈቃደኛ አልሆንም፡፡ ይሄንንም ባለመሆናችን ምክንያት ወደ ሚዲያ ሃውሶቹ በመሄድ የተለያዩ ስራዎችን ለመስራት አቅደው አንዳንድ ስራዎችን ጀምረዋል፡፡ ይሄ ደግሞ የጥፋት ስራ ነው፡፡ ጋዜጠኛውን ይዞ ወደ ጥፋት ስራ ለመግባት እየተደረገ ያለ ዝግጅት ነው፡፡ ስለዚህ ይሄንን ጋዜጠኛው እንዲያውቅ፣ እንዲነቃ፣ እንዲጠነቀቅ፣ እንዳይተባበር ለመጠየቅ ነው፡፡ ጋዜጠኞች በሽብር ተጠርጥረው ቢታሰሩ፣ በእኛ በኩል ለመሟገት ስለሚያስቸግረን ነው፡፡ ሀገር ውስጥ በህጋዊ መንገድ ተደራጅተን የምንንቀሳቀስ ስለሆንን ለመከላከልም፣ ጥብቅና ለመቆምም በኋላ ስለምንቸገር ከወዲሁ በቅድሚያ ማሳወቅ ስላለብን ነው፡፡ የእኛ አባሎቻችን አሉ፡፡ ጋዜጠኞችና የሚዲያ ሰራተኞች አሉ፡፡ እነሱ ማወቅ ስለሚገባቸው ነው፡፡ ከሽብርተኞች እና ከአሸባሪ ቡድኖች ጋር የሚደረግ ማንኛውም ዓይነት ህገወጥ ግንኙነት ዋጋ የሚያስከፍል እንደሆነ ማንም ያውቀዋል፡፡ እኛ ስለምናውቅ ህገወጡን ግንኙነት ጋዜጠኛው እንዲጠነቀቅ ብቻ ነው ያሳሰብነው፡፡ የ2007 ዓ.ም ምርጫን መምጣት ተከትሎና ከዛው ጋር በተያያዘ ስማቸውን የማንጠራቸው አገሮች አሉ፤ ወደ አገራቸው ጭምር ጋብዘውን ነበር። ያንን እኛ አልተቀበልንም፤ ነገር ግን ያንን ተቀብለው በግልፅ የሚንቀሳቀሱ አሉ፡፡ ይሄንን ጋዜጠኛው ተገንዝቦ እንዲተባበረንና ማን እንደሆነ በግልፅ ስለሚታወቅ አደጋ እንዳይመጣበት እንዲጠነቀቅ ለማሳሰብ ነው፡፡ ይሄው ነው የመግለጫው መንፈስ፡፡
የአገራቱን ስም ለመጥቀስ ያልፈለጋችሁበት ምክንያት ምንድነው?
በጥቅሉ ማድረግ የፈለግንበት ምክንያት አለ። በጥቅል ሲደረግ እና ስማቸው ሳይጠቀስ ሲቀር እጃቸውን ይሰበስባሉ፡፡ እጃቸውን ካልሰበሰቡ በቀጣይ ይፋ እናደርጋለን፡፡ እጃችሁን ሰብስቡ ይሄ የሀገር ጉዳይ ነው፤ ከሀገር (ከብሄራዊ ጥቅም) የሚበልጥ ስለሌለ ተጠንቀቁ፣ ለማለትም ጭምር ነው፡፡ ከተወሰነ ጊዜ ወዲህ ሶስቱ ማህበራት በጋራ በመሆን በየጊዜው እየተገናኘን እየተወያየንበት ነው ያለነው፡፡ በሞያው ላይ እያንዣበበ ያለ አደጋ በጋራ ለመከላከል በሚቻልበት ሁኔታ ላይ ውይይት አድርገን መስማማት ላይ ስለደረስን፣ ያንን እግረ መንገዳችንን ለመግለፅ ነው፡፡ በቀጣይ እነዚህ ችግሮች ገፍተው እንዳይሄዱ ቋሚ የሬድዮ እና ቴሌቪዥን የአየር ሰዓት ይዘን፣ እንደ ማህበር እንደ ባለሞያ ሞያውን ለማሳደግ የምንወያይበትና የምንሰራበት ሁኔታ እንዲኖር ከሚመለከታቸው ጋር ተወያይተናል፡፡ መግባባት ላይም ደርሰናል፡፡ በቅርብ ጊዜ ውስጥ ወደ ተግባር እንገባለን። ትክክለኛውን ጋዜጠኛና ነውጠኛውን መለየት ያስፈልጋል።
ታቅዶና ታስቦ እየተሰራ ያለ ነገር ነው፡፡ በማን ታቅዶ፣ በማን ተሳታፊነት እየተሰራ እንደሆነና የገንዘብ ምንጩ ማን እንደሆነ በግልፅ የምናውቀው ጉዳይ ነው፡፡ እኛ ዋናው ነገር “ለምን ቀድማችሁ አልነገራችሁንም” የሚል ነገር እንዳይመጣ ማሳሰብ ስላለብን ነው፡፡ ለሀገርና ለወገን የሚያስብ ጋዜጠኛ ይሄን ማሳሰቢያ ሰምቶ ራሱንና ወገኑን ከጥቃት የሚያድን፣ የሚጠባበቅና የሚከላከል እንዲሆን ነው፡፡ እየተደረገ ያለው ጋዜጠኞችን መከፋፈል ነው፡፡  ማህበራቸው ውስጥ ሰላም እንዳይኖራቸው መበታተን፣ ጋዜጠኞችን እርስ በርስ እያጋጩ በሚዲያ ውስጥ ያለውን ሰላምና መረጋጋት፣ በመናድና በማፈራረስ የስርጭት አድማሱን ማናጋት ነው፡፡ ከተለያዩ የሚዲያ ባለቤቶችም ጋር በዚሁ ጉዳይ ላይ ተወያይተናል በግል፡፡ ከስርጭት ጋር በተያያዘ ሰፊ አፈና አለ፡፡ እነሱ የማይፈልጉዋቸው ሰዎች በጋዜጣ እንዳይስተናገዱ፣  እንዳይወጡ፣ እንዳይፃፉ-- የስም ዝርዝር ሁሉ አዘጋጅተው እስከመስጠት የደረሱበት ሁኔታ ነው ያለው፡፡
“የሽብርና የሽብርተኛ ወገኖች፣የኢትዮጵያን ጥቅም ለመጉዳት የተሰለፉ የውጪ ሃይሎች” የተባሉት እንዲሁም ጋዜጠኛውን መጠቀሚያ ለማድረግ የሚንቀሳቀሱት እነማን ናቸው? እንዳላችሁት ጋዜጠኛውን ለማንቃት በግልፅ መናገሩ  አይሻልም ?
አሁን እጃችሁን ሰብስቡ ነው ያልናቸው፡፡ እነሱና እኛ እንተዋወቃለን፡፡ እጃችሁን ሰብስቡ ስንል ከሰበሰቡ እሰየው! ካልሰበሰቡ ደግሞ እናጋልጣቸዋለን እያልን ነው። እኛን እኮ መጥተው አነጋግረውናል፡፡ የገንዘብ ምንጩም ሁሉም ነገር ተሰጥቶናል እኮ! ያንን የቀረበልንን አማራጭ አንቀበልም ብለናል፡፡ ግን ጊዜ ይፈልጋል፡፡ ለህዝብም ለመንግስትም ይፋ እናደርጋለን፡፡ የኢትዮጵያ ጠላቶች ዙሪያችንን እያንዣበቡ ነው ያሉት፡፡ በተለያየ መንገድ ያኮረፈን፣ የተጎዳን፣ በጥቅም በመደለል ወደሚፈልጉት መስመር ለማስገባት ይሻሉ፡፡ ስለዚህ የተመቻቸ ሁኔታ እንዳይኖራቸው ጥንቃቄ ማድረግ አለብን በሚል ነው፡፡ ሰለባ እንዳንሆን ነው፡፡
የሽብርና የሽብርተኞች  ጉዳይ ከሆነ መንግስት እንዴት ዝም አለ?  
መንግስት ጋ መረጃው አልደረሰ ይሆናል፡፡ ለመንግስትም ዝርዝር መረጃ እኛ አልሰጠናቸውም፡፡ ምን አልባት እኛ ስንሰጣቸው ያዩት ይሆናላ፡፡ እጃቸውን ካልሰበሰቡ መረጃውን ለመንግስት አሳልፈን እንሰጣለን፡፡
‹‹የኢትዮጵያ ጋዜጠኞች መድረክ›› ከተባለው አዲሱ የጋዜጠኞች ማህበር ጋር በስያሜ ውዝግብ ውስጥ እንደገባችሁ ሰምቼአለሁ፡፡ እስቲ ስለእሱ ንገሩኝ----
‹‹የኢትዮጵያ ጋዜጠኞች መድረክ›› በሚል ስያሜ ወር በማይሞላ ጊዜ ውስጥ የሬድዮና የቴሌቪዥን ፕሮግራማችንን እንቀጥላለን፣ ከሁለት ዓመት በፊት የተቋረጠ ነው፡፡ ‹‹የኢትዮጵያ ጋዜጠኞች መድረክ›› በሚል ሁለት ማህበር ሊጠራ አይችልም፣ በሃገሪቱም ህግም በአሰራርም የሌለ ነገር ነው፡፡ አንቺ አዲስ አድማስ ብለሽ ጋዜጣ እየሰራሽ ከጎንሽ ሌላ ሰው መጥቶ አዲስ አድማስ ብሎ ሊሰራ አይችልም፡፡ ለማንም አሳልፈን የምንሰጠው አይደለም፡፡ ለአንድ ዓመት ኮንትራት ነበረን፣ ከኢቴቪ ጋር፡፡  ለተወሰነ ጊዜ ተላልፎ ነበር፡፡ አሁን መግባባት ላይ ተደረሰ፣ ያለው ዕውነት ይሄው ነው፡፡
በቅርቡ ‹‹የኢትዮጵያ ጋዜጠኞች መድረክ›› በሚል ስያሜ  የጋዜጠኞች ማህበር ለማቋቋም እየተንቀሳቀሱ ስላሉት ቡድኖች የምታውቁት ነገር የለም ?
ስምንት የጋዜጠኛ ማህበራት አሉ፤ በኢትዮጵያ ውስጥ፡፡ የሴት ጋዜጠኞች ማህበር፣ የአካባቢ ጥበቃ ጋዜጠኞች ማህበር፣ የጤና ጋዜጠኞች ማህበር፣ የሳይንስ ጋዜጠኞች ማህበር፣ የስፖርት ጋዜጠኞች ማህበር፣ ቀድመው የተመዘገቡና የኢትዮጵያ የሚለውን ስም የሚጠቀሙ አገራዊ ይዘት ያላቸው ግን ሶስት ናቸው። ‹‹የኢትዮጵያ ጋዜጠኞች መድረክ›› ስለሚባሉት ምንም  መረጃ የለኝም፡፡
መግለጫ ስትሰጡ ለምንድነው የግል ሚዲያውን የማትጠሩት? ለምሳሌ ባለፈው ሳምንት የመንግስት የመገናኛ ብዙሃንን ብቻ መርጣችሁ ነው መግለጫ የሰጣችሁት---
ከዚህ በኋላ በየሳምንቱ መግለጫ ስለምንሰጥ ሁሉም እንዲያውቅ እናደርጋለን፡፡ እስከ ዛሬ ክፍተት ፈጥረን ነው የቆየነው፡፡ እስከዛሬ የተለያዩ አሉባልታዎች ሲፃፉም ሲወሩም ዝም ብለን ስናይ ነበር፡፡ እንዳላየ ሆነን ችላ ብለን እናልፍ ነበር፡፡ ነገር ግን አሁን በውጪ አገር የሚሰበሰበውን ገንዘብ፤ በተለይ የሽብር ቡድኑ  ግንቦት 7 የሚያደርጋቸው እንቅስቃሴዎች መበራከትና አጠቃላይ ዙሪያ ገባ  እንቀስቃሴው ሲታይ ግን---
አሁን የሚታየው ግርግር ምርጫ ስለተቃረበ የተወሰነ የገንዘብ ድጋፍ (ፈንድ) ለማግኘት ሲባል ነው የሚሉ ወገኖች አሉ---
እኛ የፈንድ ችግር የለብንም፤ ስራ ለመስራትም፣ ስልጠና ለመስጠትም ማን እምቢ ይለናል፡፡ ጋዜጠኞችን አሰልጥኑልን ብለን እምቢ ተብለን አናውቅም፡፡
ከሃገር ውስጥ ነው ከውጪ?
ከሀገር ውስጥ ማንም እምቢ አይለንም፡፡ የውጪም ቢሆን እኛ የአለም ጋዜጠኞች ፌዴሬሽን አባላት ነን፤ ስለዚህ ጠይቀን መቀበል እንችላለን፡፡ እኛ ፈልገን ገንዘብ ያጣንበት ወቅት የለም፡፡
የጋዜጠኛ ማህበራት ብታቋቁሙም በጋዜጠኝነት ሙያ እየሰራችሁ አይደለም በሚል ትችቶች ይሰነዘርባችኋል፡፡ የት ጋዜጣ ወይም ሚዲያ ላይ ነው የምትሰሩት?
ዌብሳይት ላይ እጽፋለሁ፣ ጋዜጠኛ ነኝ እኔ፣ ወግ ብሎግ ላይ እፅፋለሁ ጋዜጠኛ ነኝ እኔ፣ ብሎገር ነኝና ጋዜጠኛ ነኝ፡፡ የት አገር ነው የፓርቲ ልሳን አባላት ጋዜጠኞች የሚባሉት። የፓርቲ አባል ሲሆኑ ያኔ  ጋዜጠኝነታቸው ያበቃል፡፡ እኛ የማንም ፓርቲ አባል አይደለንም፡፡ የሰማያዊ፣ የአንድነት ፓርቲ አባላት ተሰብስበው የጋዜጠኛ ማህበር እናቋቁም ሲሉ ይገርማል፡፡ ያቋቁሙ---- መንግስት ከፈቀደላቸው፡፡  እኛ ከልካይም ፈቃጅም አይደለንም፡፡ እኛ የራሳችንን ስራ ነው የምንሰራው፡፡
በሀገራችን ጉዳይ ላይ በጋራ ነው የምንሰራው፣ ተለያይተን አናውቅም፣ የጋራ አቋም ነው የምንይዘው፡፡ የአገር ጥቅም፣ ሰላም፣ ብሄራዊ ፀጥታ--- የሁላችንም ጉዳይ ነው፣ ስለዚህ መቼም ቢሆን ተለያይተን አናውቅም፡፡





  • ስም የማጥፋት እንቅስቃሴ መደረጉ ተገቢ አይደለም
  • ከሲፒጄ ጋራ በመሞዳሞድ የሚመጣ ለውጥም ይኖራል ብለን አናምንም
  • መግለጫ ካወጡት ማህበራትም ጋር ቢሆን ለመነጋገር በራችን ክፍት ነው

“የኢትዮጵያ ጋዜጠኞች መድረክ” በሚል ስያሜ የምስረታ ሂደቱን የጀመረው አዲሱ የጋዜጠኞች ማህበር፤ ገና ህጋዊ ፈቃዱን ባያገኝም አመራሮቹን  መርጦ በእንቅስቃሴ ላይ ይገኛል፡፡ ወደ ስምንት የሚደርሱ በጋዜጠኞች ስም የተቋቋሙ የተለያዩ ማህበራት ቢኖሩም አሁንም ድረስ የጋዜጠኞች መብትም ሆነ የፕሬስ ነፃነት አለመከበሩን የአዲሱ ማህበር አመራሮች ይናገራሉ፡፡ የተቋቋሙት ማህበራትም ጋዜጠኞች ሲታሰሩ ድምፃቸውን አሰምተው አያውቁም የሚሉት አመራሮቹ፤ ለጋዜጠኞች ተቆርቋሪ የሆነ፣ ለመብታቸው የሚታገልላቸው ማህበር ያስፈልጋል በሚል ተሰባስበው፣ አዲሱን ማህበር የመመሥረት እንቅስቃሴ መጀመራቸውን ገልፀዋል፡፡  የአዲስ አድማስ ጋዜጠኛ አበባየሁ ገበያው የኢትዮጵያ ጋዜጠኞች መድረክ ፕሬዚዳንት አቶ በትረ ያቆብንና የህዝብ ግንኙነት ሃላፊውን አቶ ዘሪሁን ሙሉጌታን በማህበሩ ዓላማ፣ ሦስቱ የጋዜጠኞች ማህበር ሰሞኑን ባወጡት አነጋጋሪ መግለጫ ዙርያና ሌሎች ጉዳዮች ላይ አነጋግራቸዋለች፡፡  

“የኢትዮጵያ ጋዜጠኞች መድረክ” በሚል ስያሜ አዲስ የጋዜጠኛ ማህበር ለማቋቋም በእንቅስቃሴ ላይ ናችሁ፡፡ በአገሪቱ ውስጥ ስምንት የጋዜጠኞች ማህበራት እያሉ አዲስ ማህበር የማቋቋም ፋይዳው ምንድነው?
በትረ ያዕቆብ- አሁን ባለው ሁኔታ፣ የጋዜጠኞች መብት አልተከበረም፡፡ አሁን ባለው ሁኔታ፣ የፕሬስ ነፃነት እየተከበረ አይደለም፡፡ ጋዜጠኛው ሀሳቡን በነፃ የመግለፅ መብቱ አልተከበረለትም፡፡ የጋዜጠኛ ማህበራቱ ተቋቋሙ እንጂ እነዚህን ችግሮች በቅጡ መፍታትም ሆነ ለጋዜጠኞች ሊታገሉላቸው አልቻሉም፡፡ ይሄ ሁሉ ጋዜጠኛ ሲታሰር ሲፈታ፣ ድምፃቸውን አሰምተው አያውቁም፡፡ ጋዜጠኞች ሲታሰሩም ለምን ሲሉ አንሰማም፡፡ ስለዚህ የሆነ፣ ክፍተት አለ ማለት ነው፡፡  እኛ የመጣነው ያንን ክፍት ለመሙላት ነው፡፡ ለጋዜጠኞች ተቆርቋሪ የሆነ፣ ለጋዜጠኞች የቆመ ማህበር ያስፈልጋል፡፡ ለጋዜጠኞች ታማኝ የሆነ ነፃ፣ ገለልተኛና ለማንም ያልወገነ ማህበር ያስፈልጋል ብለን ነው ማህበሩን ለማቋቋም የተሰባሰብነው፡፡
በፊትም የጋዜጠኛ ማህበር የማቋቋም ፍላጎቱ ነበረን። በተለይም በቅርቡ በ “ኢትዮ ምህዳር” ጋዜጠኞች ላይ የደረሰውን አደጋ ተከትሎ በተለይም የመኪና አደጋ በደረሰበት ኤፍሬም ምክንያት ነው መነቃቃቱ የተፈጠረው። “ለምን አሁን አይሆንም?” በሚል ተሰባሰብን፡፡
ዘሪሁን ሙሉጌታ - የጋዜጠኞች ማህበር የማቋቋም ፍላጎቱ በየኮሪደሩ ነበር፡፡ ነገር ግን ኤፍሬም አደጋ በደረሰበት ወቅት ምንም ያህል ብንሮጥ የሚታከምበት ገንዘብ ማግኘት አልተቻለም፡፡ ጋዜጠኞች በወቅቱ “ለካ የሚደርስልን የለም፣ ለእኛ የሚቆም የለም” በማለት ተደናገጡ፡፡ ማህበር ቢኖረን እኮ ይሄ ሁሉ ችግር አይኖርብንም፤ ጠንካራ ማህበር ያስፈልገናል፤ የሚል ሀሳብ መጣ፡፡ የተወሰኑ ልጆች ይሄንን የተቀሰቀሰ ሀሳብ በአጀንዳነት ይዘው መምከር ያዙ፡፡ በመቀጠል ጊዜያዊ ኮሚቴ ተቋቋመ፡፡ ጥናቶች ተደረጉ፤ በኋላም ማህበራችን እንደዚህ አይነት ቅርጽ ሊኖረው ይገባል ብለን እንቅስቃሴውን ሊመሩ ይችላሉ ያልናቸውን ስምንት ሰዎችን መረጥን፡፡
ከምስረታችሁ ጋር በተያያዘ ከበስተጀርባችሁ ግፊት የሚያደርጉ ወገኖች እንዳሉ ይነገራል፡፡ በዚህ ጉዳይ ላይ ምን ትላላችሁ?
በትረ - በስተጀርባችን ምንም አካል የለም፡፡ የተሰባሰብነው ጋዜጠኞች ነን፣ በሞያችን የሚገጥሙንን ችግሮች ለመጋፈጥ በሚል ነው ማህበር ለማቋቋም የተነሳነው፡፡ በጋዜጠኛው ላይ ተፅዕኖ የሚያሳርፈው መንግስት ብቻ አይደለም፤ የእምነት ተቋማት ተፅዕኖ ያሳድሩበታል፤ ሌሎችም አሉ፣ ጋዜጠኛውን ከእነሱ ለመጠበቅ  ነው ዓላማችን፡፡  
ዓለም አቀፉ የጋዜጠኞች ማህበር ሲፒጄ ከየሚዲያው ጋዜጠኞችን በማሰባሰብ አሁን ያሉትን ሶስት ማህበራት ማለትም ኢብጋህ፣ ኢገማ፣ ኢነገማን ስለማላምናቸው አዲስ ማህበር አቋቁሙ ብሏችሁ ነው የተሰበሰባችሁት የሚባል ወሬ ይናፈሳል..
በትረ- መሠረት የሌለው ነገር ነው፡፡ የተቋቋምነው ራሳችን ተሰብስበን ነው፡፡ ሲፒጄን ማን እንዳመጣው አናውቅም፡፡ አላስፈላጊ ነገር እየተወረወረብን ነው፡፡ ገና ሊቋቋም ያለ ማህበር ማጠልሸት ለምን እንዳስፈለገ አናውቅም፡፡ የተሰባሰብነው ከሚደርስብን ጥቃት ራሳችንን ለመጠበቅ ነው፡፡ ለጋዜጠኞች ድምፅ ለመሆን ነው፡፡ ከበስተጀርባችን ድብቅ አላማ ያለው፤ የደገፈንም አካል የለም፡፡ ነገ ከነገ ወዲያ አብረውን ሊሰሩ የሚፈልጉ አካላት ሊኖሩ ይችላሉ፤ መንግስትም አንዱ አካል ነው፡፡ በተረፈ ሌላውን እንደ አሉባልታ ነው የማየው፡፡
ዘሪሁን- ሲፒጄ ማንዴትም የለውም፤ ጋዜጠኞችን ኢትዮጵያ ውስጥ የማደራጀት፣ የመምራት፣ የማስተባበር ማንዴትም የለውም፡፡ እኛ ጋዜጠኞች ነን፣ ብዙ ነገር እናውቃለን፡፡ የሀገሪቱን ህግ ጠንቅቀን የምናውቅ ነን፡፡ ከሲፒጄ ጋራ በመሞዳሞድ የሚመጣ ለውጥም ይኖራል ብለን አናምንም፡፡ ዝም ብሎ አሉባልታ ነው፡፡ ይሄን ማህበር ለየት የሚያደርገው በራሳቸው በጋዜጠኞች ተነሳሽነት፣ ችግሩንም ተጋፋጭ እንደሆኑ አምነው የፈጠሩት ስብስብ መሆኑ ነው፡፡ በዚህ ደረጃ መፈረጁ በጣም የሚያሳዝን ነው፡፡ እንዲህ መፈራረጁም ነው ጋዜጠኞችን ትክክለኛ ማህበር እንዳይኖረን የሚያደርገን። አሁንም ዳር ሆኖ አቃቂር ማውጣቱ ስለማይጠቅም እንደውም ጋዜጠኞች መጥተው በግልፅ እንዲሳተፉና የራሳቸውን አስተዋፅኦ እንዲያበረክቱ እንጠይቃለን፡፡
ምርጫ ካደረጋችሁ በኋላ በአመራርነት ላይ የተቀመጡት የፓርቲ ልሣናት ላይ የሚሰሩ፣ የፖለቲካ ፓርቲ  አባል የሆኑ ናቸው የሚባለውስ ?
በትረ- አዎ የፓርቲ ልሣን ላይ የሚሰሩ ሰዎች በመሃላችን አሉ፡፡ የፓርቲ ልሣን ላይ ስለሚሰራ የጋዜጠኝነት ሞያ አይተገብርም ማለት የሚቻል ግን  አይመስለኝም፡፡ የመንግስት ልሣን ላይ የሚሰራ ጋዜጠኛ ነገ በአባልነት ቢመጣ እየተገበረ ባለው ሞያ ከለላ የሚያስፈልገው ከሆነ፣ የእኛ ማህበር እጁን ስሞ ነው የሚቀበለው፡፡ እኛ የምንፈልገው የማህበራችን መርሀግብሮች እና ዓላማ ላይ ያላቸውን እምነት ብቻ ነው። በተረፈ ማንንም ጋዜጠኛ እንቀበላለን፡፡ ልሣንም ላይ ይስሩ …ምንም ይስሩ፣ በሚሠሩት ስራ ከሞያቸው አንፃር ከለላ ያስፈልጋቸዋል፤ እነሱን መጠበቅ የማህበራችን ዓላማ ነው፡፡
ዘሪሁን- ሀሳብን በነፃነት የመግለፅ መብት ይከበር እያልን፣ አንድ ሰው በያዘው የፖለቲካ አመለካከት የተነሳ በጋዜጠኞች ማህበር ውስጥ አትገባም በሚል መከልከል አንችልም፡፡ ዋናው ነገር የያዘውን የፖለቲካ አስተሳሰብ ማህበሩ ላይ እንዳይጭን መከላከል ነው፡፡ ከዚህ ቀደም የነበሩ ማህበራት ስህተት ከባህሪያቸው፣ የአንድ የፖለቲካ ፓርቲ ባህሪ ያላቸው መሆናቸው ነው፡፡ የአንድ የፖለቲካ ፓርቲ ባህሪ፣ ስልጣን ለመያዝ የሚታገል ነው፡፡ ማህበር ግን የአባላቱን ጥምቅ ማስከበር እንጂ ስልጣን መያዝ አይደለም ግቡ፤ እኛ እየመሰረትን ያለው የጋዜጠኞች ማህበር መድረክ የቆመው ስልጣን ለመያዝ ሳይሆን፤ በአገሪቱ ያሉ የጋዜጠኞችን መብት ለማስከበር፣ የሀሳብ ነፃነትን እንዲረጋገጥ ለመታገል ነው፡፡ የአብዮታዊ ዲሞክራሲ ልሣን፣ የኢህአዴግ ልሣን ነው፡፡ በዛ ውስጥ ተቀጥረው የሚሰሩ በእኛ ማህበር ሀሳብ የሚስማሙ ከሆነ እነሱም በአባልነት እንይዛለን፡፡ ኢትዮጵያ ውስጥ ሀሳብን በነፃ የመግለፅ ነፃነትና የጋዜጠኞች መብት አልተከበረም የሚል አቋም አለን፡፡ ይህን የሚያምን የአብዮታዊ ዲሞክራሲ፣ የኢቴቪ ጋዜጠኛ ካለ በአባልነት እንቀበላለን፡፡ ይኼው አመለካከታችን ተቃዋሚ ፓርቲ ላይ ቢሰራ ለምንድን ነው ልዩ የሚሆነው? የተቃዋሚዎችን አላማ በማህበራችን ላይ እንዳይጭን ግን  እንጠብቃለን፡፡ በጉባዔው ላይ አንድም ያከራከረን ይሄው ነበር:: የመንግስትና የግል ጋዜጠኛ የሚል ሀሳብ ተነስቶ በስፋት ተወያይተንበታል፡፡ ይሄ ማህበር በጋዜጠኝነት ሞያ አማራጭ ዘርፎች ማለትም በብሎገርነትም፣ በኤሌክትሮኒክስ ሚዲያ፣ በጋዜጣም ያሉ ሀሳብን በመግለፅ እንቅስቃሴ ውስጥ ተሳታፊ የሆኑትን በሙሉ ያቅፋል፡፡
ማህበራችሁ የግልንም የመንግስትንም ጋዜጠኞች ያቀፈ ነው ማለት ነው?
እስካሁን የመንግስት ሚዲያ ላይ ከሚሰሩት መካከል በድፍረት መጥቶ ማህበሩን የተቀላቀለ የለም፡፡ ወደፊት አላማውን ሲረዱ ሊመጡ ይችላሉ፡፡
በኢትዮጵያ ስምንት የጋዜጠኞች ማህበራት አሉ። እናንተ ከእነዚህ ማህበራት ጋር ያላችሁ ግንኙነትና መስተጋብር ምን ይመስላል? በተለይ ሶስቱ ማህበራት ኢብጋህ፣ ኢነጋማና ኢገማ የተባሉት ሰሞኑን መግለጫ አውጥተዋል፡፡ የኢትዮጵያ ጋዜጠኞች ከሽብርና ከሽብርተኞች ተጠንቀቁ የሚል፡፡ መግለጫውን እንዴት አገኛችሁት?
በትረ- እኛ እነሱን የምንላቸው እህት ማህበራት ነው፡፡ ፅንፍ መያዝ የትም አያደርስም፡፡ እኛ የፖለቲካ ጥያቄ አይደለም የምናነሳው፡፡ እየመሰረትን ያለነው የሞያ ማህበር ነው፡፡ ስልጣንም አይደለም ጥያቄያችን፡፡ ጥያቄያችን፤ ሀሳብን በነፃ የመግለፅ መብት መከበር አለበት የሚል ነው፡፡ ጋዜጠኛ በጋዜጠኝነቱ ሊታሰር፣ ሊደበደብ፣ ሊሰደብ ወይንም ዛቻ ሊቀርብበት አይገባውም ነው የምንለው፡፡ ይሄን ለማስተካከል ፅንፍ መያዝ አይገባም። ከሁሉም አካል ጋር በመስራት ነው የሚፈታው፡፡ ሁሉም አካል ስንል መንግስትንም ይጨምራል፡፡ ፅንፍ መያያዙ የትም አያደርሰንም ነው የምለው፡፡ ፅንፍ መያዝ ለቆምንለት አላማ ግብ መምታት ፋይዳ የለውም፡፡ የሚያዋጣን፤ ባሉት ችግሮች ላይ መወያያት፣ መፍትሄ ማቅረብ ነው፡፡ ከእነሱ ጋርም ቢሆን ለመነጋገር በራችን ክፍት ነው፡፡
የጋዜጠኞች ማህበራቱ በመግለጫቸው፤ በሽብርተኝነት የተፈረጁ አካላት ጋዜጠኞችን ለመጠቀም ጥረት እያደረጉ ነው ብለዋል ---
በትረ- ማህበራችን ነፃና ገለልተኛ ነው ስንል ራሳችንን የምንጠብቀውና ነፃነታችንን የምናስጠብቀው ከመንግስት የሚደርስብንን ተፅዕኖ በመቋቋም ነው፡፡ ነገር ግን ተፅዕኖው ከፖለቲካ ፓርቲዎችም ሊመጣ ይችላል፡፡ ተፅዕኖውን ለመፍጠር ፍላጎቱ ያላቸው ቡድኖች አሉ፡፡ እኛ ግን ከዚህ ገለልተኛ ሆነን የምናራምደው የጋዜጠኞችን መብት ነው፡፡ ሌላው ነገር አሉባልታ ነው፤ እኛ ጋዜጠኞች ነን፡፡ የዚህ አገር ዜጎች ነን፡፡
ዘሪሁን- ይሄ ውንጀላ በጣም የሚያሳዝን ነው፡፡ እኛን ያውቁናል፡፡ እኛ የምንፅፈውን ነገር የሚያነቡ ሰዎች ናቸው፡፡ አሉባልታ ነው፡፡ መብት ለማስከበር ፍላጎት ያላቸው ጋዜጠኞች ተነስተው ማህበር ለመመስረት እንቅስቃሴ ሲጀምሩ መወንጀላቸው ተገቢ አይደለም፡፡ በመቋቋም ላይ ያለን ሰዎች ነን፡፡ ጣቢያውም በእንደዚህ አይነት ነገር ተባባሪ በመሆኑ እና ስም የማጥፋት እንቅስቃሴ መደረጉ ተገቢ አይደለም፡፡ ይህ ስለተባለ ደግሞ የሚያስበረግግ፣ የሚያስደነግጥ ነገር አይሆንም፡፡ ጋዜጠኛውም ይህንን በደንብ ያውቀዋል፡
በትረ- አዲስ ማህበር ሲመጣ ቢቻል ማበረታታት፣ ድክመቶች ሲታይ ገንቢ በሆነ መንገድ አስተያየት መስጠት ይገባል፡፡ ከዛ አልፎ ግን ሰዎችን ጽንፍ ማስያዝ፣ ያልሆነ ስም መለጠፍ ጤናማ አይደለም፡፡
ዘሪሁን- ማህበር ያቋቋማችሁት ለመሰደድ ነው ተብለናል፡፡ ማህበሩ ከተቋቋመ በኋላ ብዙ ነገሮች እንሰማለን፡፡ እርግጥ ነው፤ ማህበር የሚባል ነገር ሲመሰረት እንደዚህ ዓይነት ነገሮች ይመጣሉ ተብሎ ይገመታል፡፡ አሁን ግን ባልገመትነው መጠንና ሁኔታ ነው እየተናፈሰ ያለው፡፡ ለመሰደድ ከተባለ ኢትዮጵያ ውስጥ..እኛ እንደውም ሳንሰደድ በስማችን ብዙ ጋዜጠኛ ነው የሚሰደደው፡፡ በጣም የተበላሸ አሰራር እንዳለ እናውቃለን፡፡ በጣም ጠንካራና እንደዚህ ዓይነት ማህበር መኖሩ በእኛ ስም የሚነገደውን መላ ለማስያዝ አንድ መስመር ነው የሚሆነው፡፡ ለመሰደድ ለመሰደድማ እንኳን ጋዜጠኛ፣ እህቶቻችን የቤት ሠራተኛ ለመሆን ይሰደዱ የለ፡፡
በአመራር ምርጫ ወቅት አንዳንድ ችግሮች ተስተውለዋል የሚባል ነገር ሰምቻለሁ …
ምርጫው ፍፁም ዲሞክራሲያዊ ነበር፡፡ በታዛቢዎች፣ ገለልተኛ የነበሩ ሰዎች ባሉበት የተካሄደ ምርጫ ነው፡፡ እኔ ካልመራሁት ብሎ በማህበሩ ላይ ቅር በመሰኘት የሚወጣ ሰው ሊኖር ይችላል፡፡ ሂደቱ ውጣ ውረድ የነበረው ቢሆንም አሁን  እንደ ማህበር ቆሟል፡፡
ምርጫውን የታዘቡ ገለልተኛ አካላት የተባሉት እነማን ናቸው?
ዘሪሁን- ኤምባሲዎች መታዘብ ፈልገው መጥተው ታዝበዋል፡፡ የእንግሊዝና አሜሪካ ኤምባሲዎች መጥተው ነበር፡፡
ስንት አባላት አሉዋችሁ?
በትረ- ወደ 30 የሚሆኑ አባላት አሉን፡፡ በተባባሪ፣ በክብር አባልነት የምንይዛቸው ይኖራሉ፡፡
የአጭር ጊዜና የረጅም ጊዜ እቅዳችሁ ምንድን ነው?  
የሶስት ወርና የስድስት ወር እቅድ አለን፡፡ ማህበሩ እውቅና እንዲያገኝ እንሰራለን፡፡ ልናቋቁመው የፈለግነው ተቋም ነው፡፡ የሚያስፈልጉትን መረጃዎች እያዘጋጀን ነው። የፕሬስ ነፃነትን ፕሮሞት በማድረግ ረገድ ያዘጋጀናቸው ነገሮች አሉ፡፡
ሜይ 3 ‹‹የአለም የፕሬስ ነፃነት›› ቀንን ልናከብር የስድስት ወር እቅድ ይዘናል፡፡ ቀኑን በተለያዩ ዝግጅቶች ለማክበር ተሰናድተናል፡፡ የእግር ጉዞ፣ የሻማ ማብራት፣ ኮንፍረንስ አድርገን እለቱን እንዘክረዋለን፡፡
የገንዘብ ምንጫችሁ ምንድነው?
የገንዘብ ምንጭ ብለን የያዝነው አባላቱን ነው፡፡ አዲስ ማህበር እንደመሆኑ በዓመት የሚከፈል የአባላቱ ክፍያ፣ የመመስረቻ ክፍያ፣ የገቢ ማሰባሰቢያ የራት ምሽት …  ለጊዜው እኒህ ናቸው፡፡

ኪሳራው በጊዜ ሲሰላ፣ የአገሪቱን የስልጣኔ ጭላንጭል ያዳፈነ፣ የ30 ዓመት የኋሊት ጉዞ ነው።
30 ዓመት ቀላል አይደለም፤ እነ ደቡብ ኮሪያ ከድህነት ወደ ብልፅግና የተሸጋገሩበት ጊዜ ነው።
“የአብዮተኛው ትውልድ”ን ኪሳራዎችን ለመደበቅ ተብሎ ብዙ ታሪክ ተድበስብሷል
ትምህርት የተስፋፋው፣ የሴት ተማሪዎች ቁጥር ያደገው ከአብዮቱ በፊት ነው ወይስ በኋላ?
የኤሌክትሪክ፣ የስልክ፣ የመንገድና የአየር ትራንስፖርት በፍጥነት የተሻሻለውስ መቼ ነው?
በእህል ምርት፣ በኢንዱስትሪ፣ በኤክስፖርት መስኮች የብልፅግና ምልክት የታየውና የጠፋውስ?
የሙያ ፍቅር ያበበው፤ ስነፅሁፍ፣ ትያትርና ሙዚቃ ያደገው፤ ስፖርት የተሻሻለው መቼ ይሆን?

በ1950 ዓ.ም በአዲስ አበባ፣ ከተለያዩ የአገሪቱ ክፍል የመጡ የከፍተኛ ሁለተኛ ደረጃ ተማሪዎች ላይ የዳሰሳ ጥናት ያካሄዱት ዊሊያም ሻክ፤ በአገሪቱ እያቆጠቆጠ ከመጣው የትምህርትና የስልጣኔ ጅምር ጋር መልካም የአስተሳሰብ ለውጥ እየመጣ እንደነበር ይገልፃሉ። አንደኛ፤ የዘመኑ ወጣቶች እንደ ጥንቱ የመንግስት ስልጣንንና ተቀጣሪነትን አልያም የሃይማኖት መሪነትንና ሰባኪነትን የሚመኙ አይደሉም። ሁለተኛ፤ “ይሄኛው ሙያና ይሄኛው የሕይወት ዘይቤ፣ ለአማራ፣ ለኦሮሞ ወይም ለሶማሌ ተወላጅ ነው። ያኛው ሙያና ያኛው የኑሮ ዘይቤ ደግሞ ለትግራይ፣ ለወላይታ ወይም ለጉራጌ ተወላጅ ነው” የሚሉ የዘልማድ አዝማሚያዎችን አይቀበሉም። የ1950ዎቹ ወጣቶች የሙያና የግል ሕይወታቸውን በራሳቸው መንገድ መምራት እንደሚችሉ የሚያምኑ ሆነዋል።
ተማሪዎቹ ከተለያዩ የአገሪቱ አካባቢዎች የመጡ ቢሆኑም፤ የሙያ ምርጫቸው ይመሳሰላል። ከመንግስት ስልጣንና ተቀጣሪነት ወይም ከሃይማኖት ሰባኪነት ይልቅ፤ ከሁሉም በላይ ቅድሚያ የሚሰጡት ለምህንድስና ወይም ለህክምና ሙያ፣ ለሜካኒክነት ወይም ለአስተማሪነት ሙያ እንደሆነ ጥናቱ ገልጿል። በአጭሩ፤ በያኔው የስልጣኔ ጭላንጭል፤ ለእውቀትና ለሳይንስ፤ ለሙያዊና ለምርታማ ስራ ክብር የሚሰጥ ትውልድ እየተፈጠረ ነበር። በአገሪቱ እየታየ የነበረውንም የትምህርትና የኢኮኖሚ ብሩህ አቅጣጫ ያመላክታል። Occupational Prestige, Status, and Social Change in Modern Ethiopia: William A. ShackSource: Africa: Journal of the International African Institute, Vol. 46, No. 2 (1976), pp. 166-181
በ1950ዎቹ ዓ.ም ኢትዮጵያ በሁሉም መስኮች ከእንቅልፏ እየነቃች እንደነበረ የሚያሳዩ የጥበብ ስራዎችንም መጥቀስ ይቻላል። የሃዲስ አለማየሁና የፀጋዬ ገብረመድህን ድርሰቶች፣ የነጥላሁን ገሠሠና የነምኒልክ ወስናቸው የሙዚቃ ስራዎች፣ ዛሬ ከአርባ እና ሃምሳ አመታት በኋላም፣ ወደር አልተገኘላቸውም። በእግር ኳስ እና በሩጫ ስፖርቶችም እንዲሁ።
በመንግስት አስተዳደር በኩልም፤ ትልቅ “የስልጣኔ አብዮት” የተካሄደው፣ ከ1960ዎቹ “አብዮተኛ ትውልድ” በፊት ነው። ለሺ አመታት በሃይማኖታዊ ሰነዶች (በክብረ ነገስትንና በፍትሃ ነገስት) ላይ ተመስርቶ የቆየውን የአገሪቱ ሥርዓትና ሕግ፣ ከኋላቀርነት ለማላቀቅና የስልጣኔ እድል ለመፍጠር ያስችላሉ የተባሉ የሕገመንግስት እና የምርጫ ህጎች ከ1923 እስከ 1948 ዓ.ም ፀድቀዋል። የተለያዩ የፍትሐ ብሄርና የወንጀል ሕጎች ከ1935 እስከ 1960ዎቹ መግቢያ ድረስ ታውጀዋል። የወንጀልና የፍትሐ ብሄር ህጎቹ እስከ ዛሬ ድረስ ይሰራሉ - (በ2000 ዓ.ም የተወሰነ ማሻሻያ ቢታከልባቸውም)።
ነገር ግን ሕጎችን በማወጅ ብቻ ሳይሆን፤ በግል አርአያነትና ጥረትም አገሬውን ወደ ስልጣኔ ለማራመድ ሙከራዎች ተደርገዋል። “በለውጥ ላይ የምትገኝ ኢትዮጵያ” በሚል ርዕስ በ1948 ዓ.ም ጥናታዊ ፅሁፍ ያቀረቡ ሲሞን ሜሲን፤ በ1925 ገደማ ዓ.ም የንጉሡ ሴት ልጅ መሞቷን ጠቅሰው፤ ለሟቿ ልዕልት የተዝካር ድግስ እንደማይዘጋጅ በአዋጅ መነገሩን ይገልፃሉ። ኢትዮጵያውያን ገበሬዎች ያለ አቅማቸው በሚደግሱት ተዝካር ኑሯቸው መናጋቱ ብቻ አይደለም ችግሩ። የየአካባቢው የመንግስት ባለስልጣናት በየፊናቸው ተዝካር ሲደግሱ፤ የአካባቢው ነዋሪና ገበሬ፤ ወደደም ጠላም፤  እህል፣ ከብት እና ገንዘብ እንዲያዋጣ ይገደዳል። ገበሬዎችን ከዚህ ልማዳዊ ሸክም ለመገላገል ነበር የንጉሡ ሙከራ - ይላሉ ፀሐፊው።
ይህም ብቻ አይደለም። የድሮ ለቅሶ እንደዛሬ አይደለም። በእርግጥ ዛሬም ቢሆን፤ የአገራችን ለቅሶ ለታይታ የሚቀርብ ቅጥ ያጣ ልማድ ነው። ግን የድሮው ይብሳል። ሰው ሲሞት፣ ልብስ መቅደድና ፀጉር መንጨት፤ ፊት መቧጨርና ደረት መደለቅ፤ መሬት ላይ መንከባለልና አፈር መልበስ የተለመደ ነበር። ነውጠኛ ለቅሶ ይሉሃል ይሄ ነው። ይህን ለማስቀረት ንጉሡ እንደጣሩ የሚገልፁት ሲሞን ሜሲን፤ ነጠላ አዘቅዝቆ መልበስ የተጀመረው ያኔ ነው ይላሉ። Changing Ethiopia፡ Simon D. MessingSource: Middle East Journal, Vol. 9, No. 4 (Autumn, 1955), pp. 413-432።
እንዲህ በየመስኩ የስልጣኔ ጭላንጭሎች ብቅ ብቅ ቢሉም፤ የ1960ዎቹ ተማሪዎችና ወጣት ምሁራን፤ በንጉሡ ደስተኛ አልነበሩም። እንዲያውም፤ ንጉሡን እንደ ዋነኛ ጠላት ፈርጀዋቸዋል። “ንጉሡ አገሪቱን በኋላቀርነት አስረው ይዘዋል። ህዝቡን ከትምህርት አራርቀውታል፤ በተለይ ሴቶች በመሃይምነት ጨለማ ተውጠዋል (ድርብ ጭቆና እንዲሉ)።  ህዝቡ ከመሰረተ ልማትና ከኢኮኖሚ እድገት፣ ከኤሌክትሪክና ከስልክ፣ ከመንገድና ከትራንስፖርት አገልግሎቶች እንዳይተዋወቅ፤ የእርሻና የኢንዱስትሪ እድገት እንዳያይ ያደረጉት ንጉሡ ናቸው” የሚሉ ውግዘቶች፤ በያኔዎቹ “የአብዮታዊ ትውልድ” አባላት እንደተጀመሩ እስከዛሬ ዘልቀዋል።
እውነታው ግን፤ ሙሉ ለሙሉ የዚህ ተቃራኒ ነው። በእርግጥ፤ የንጉሡን ዘመን በብዙ ምክንያቶች መተቸት ይቻላል። “የአገሪቱ የስልጣኔ ጅምር ተንቀራፈፈ፤ መፍጠን ነበረበት” ብሎ መተቸት ስህተት አይሆንም። በአብዮቱ የመጣው ለውጥ ግን፤ ጭራሽ የስልጣኔ ጅምርን አዳፍኖ የሚደመስስ ሆነ። ከንጉሡ ድክመት ይልቅ “የአብዮታዊው ትውልድ” ጥፋት በብዙ እጥፍ ይልቃል። “የአብዮታዊው ትውልድ” በርካታ አባላት ታዲያ፣ ይህ ታሪካዊ ውድቀታቸውና ኪሳራቸው በግልፅ እንዲታወቅ አይፈልጉም። ለዚህም ነው፤ እንደያኔው አሁንም ጨምር፤ የንጉሡን አስተዳደር ከማውገዝና ከማጥላላት ያልቦዘኑት። ነገር ግን እውነታውን ለዘላለም መሸፈን አይችሉም። የንጉሡንና የአብዮቱን ዘመናት፤ የዛሬውንም ጭምር ለመመዘንና ለማነፃፀር የምንችልባቸው መረጃዎች ብዙ ናቸው። ዛሬ ጥቂቶቹን ብቻ እንመልከት።      

ትምህርት ከጀማሪ እስከ ዩኒቨርስቲ
በ1938 ዓ.ም የአንደኛና የሁለተኛ ደረጃ ተማሪዎች ቁጥር፣ 35ሺ እንደነበር የሚገልፁት ዶ/ር ተከስተ ነጋሽ፣ ከአስር አመት በኋላ 95ሺ እንደደረሰ ይገልፃሉ - ዘጠኛ ሺ ገደማ የአንደኛ ደረጃ፣ አራት ሺ ገደማ የሁለተኛ ደረጃ፣ አራት መቶ ገደማ የከፍተኛ ትምህረት ተማሪዎች። በ1955 ዓ.ም፣ የሁለተኛ ደረጃ ተማሪዎች አስር ሺ፣ የአንደኛ ደረጃ ተማሪዎች ደግሞ 305 ሺ መድረሱን ዶ/ር ተከስተ ጠቅሰዋል - በወቅቱ የስምንተኛ ክፍል ተማሪ እንደነበሩ በማስታወስ Education in Ethiopia Nordiska Afrikainstitutet, Uppsala። እንደገና ከአስር አመት በኋላ በአብዮቱ ዋዜማ፣ የአንደኛ ደረጃ ተማሪዎች ቁጥር 1.04 ሚሊዮን ደርሷል - በሃያ አመታት ውስጥ ከአስር እጥፍ በላይ በማደግ።
በደርግ ዘመን፣ በአንደኛ ደረጃ ትምህርት የተመዘገበው የተማሪዎች ቁጥር ወደ 2.9 ሚሊዮን ገደማ ነው - በሶስት እጥፍ አድጓል ማለት ነው። በኢህአዴግ 20 አመታት ውስጥስ? የተማሪዎቹ ቁጥር ወደ 15 ሚሊዮን ገደማ ሆኗል። በደርግ ዘመን ከነበረው ቁጥር ጋር ሲነፃፀር በአምስት እጥፍ ይበልጣል።
በንጉሡ ዘመን በሃያ አመታት ውስጥ ከሃያ እጥፍ በላይ የጨመረው የሁለተኛ ደረጃ ተማሪዎች ቁጥር በ1966 ዓ.ም 190ሺ ገደማ እንደደረሰ የሚገልፀው የአለም ባንክ መረጃ፣ በደርግ ዘመን ወደ 900ሺ እንደተጠጋ ይገልፃል። የደርግ ዘመን የተመዘገበው የአራት እጥፍ እድገት ከንጉሡ ዘመን ያነሰ ነው። በኢህአዴግ ጊዜም እንዲሁ። ኢህአዴግ ደግሞ በሃያ አመታት ውስጥ ወደ አምስት እጥፍ ገደማ በማሳደግ 4.5 ሚሊዮን አድርሶታል።
የከፍተኛ ትምህርት ተማሪዎች ቁጥር፣ በንጉሡ ዘመን በሃያ አመታት ውስጥ፣ ከአራት መቶ ገደማ ወደ 6500 አካባቢ ጨምሯል -  በአስራ አምስት እጥፍ። በደርግ ዘመን ወደ ሶስት እጥፍ ገደማ አድጎ 18ሺ የደረሰ ሲሆን፣ በኢህአዴግ የሃያ አመታት ጊዜ፣ እንደ ንጉሡ ዘመን ከአስራ አምስት እጥፍ በማደግ ከ350ሺ በላይ ሆኗል።

ትምህርት በወንዶችና በሴቶች
የአብዮተኞቹ አንዱ መፈክር፣ የፆታ እኩልነት የሚል አልነበር? እስቲ የሴት ተማሪዎችን ድርሻ እንመልከት። አብዮተኞቹ የንጉሡን ዘመን ሲያወግዙ ስትሰሙ፤ በአብዮቱ ዋዜማ በአንደኛ ደረጃ ትምህርት፣ የሴቶች ድርሻ ከዜሮ በታች የነበረ ነው የሚመስላችሁ። ነገር ግን፣ የትምህርት ሚኒስቴር መረጃ እንደሚያመለክተው፣ በ66 ዓ.ም. ከአንደኛ ደረጃ ተማሪዎች መካከል 32 በመቶ ያህሉ ሴቶች ነበሩ። በደርግ ዘመን የሴቶች ድርሻ ወደ 40 በመቶ ገደማ ደረሰ፣ በኢህአዴግ ደግሞ ወደ 47 በመቶ።
በከፍተኛ ትምህርት፣ እዚህ ግባ የማይባል ድርሻ የነበራቸው ሴቶች፣ በ1952 ዓ.ም ወደ 3 በመቶ ድርሻ ካገኙ በኋላ፣ በሶስት እጥፍ አድጎ በአብዮቱ ዋዜማ ወደ አስር በመቶ ገደማ ድርሻ ለመያዝ የበቁ ሲሆን፣ በደርግ ዘመን የሴቶች ድርሻ ወደ 18 በመቶ አድጓል። በኢህአዴግ ዘመን ደግሞ፣ ወደ 30 በመቶ ገደማ ደርሷል።
በሴቶች ትምህርት ዙሪያ ፈጣን እድገት የተመዘገበው መቼ እንደነበር፤ ይሄው መረጃው ራሱ ይናገራል።
የቴክኒክና ሙያ ትምህርት ላይም አብዮተኞቹ ለውጥ አላመጡም። በንጉሡ ዘመን፣ በመጨረሻዎቹ ሃያ አመታት፣ የቴክኒክና ሙያ ትምህርት ከሰላሳ እጥፍ በላይ ስለጨመረ፣ የተማሪዎቹ ቁጥር በአብዮቱ ዋዜማ 8700 ገደማ ደርሶ ነበር። በደርግ ዘመን የታየው እድገት ኢምንት ነው። የተማሪዎች ቁጥር ከአስር ሺ ብዙም ፈቀቅ አላለም። በመጀመሪያዎቹ የኢህአዴግ አስር አመታትም እንዲሁ፣ የእድገት ፍንጭ አልታየም። ከዚያ በኋላ ነው በፍጥነት ማደግ የጀመረው። በኢህአዴግ ሃያኛ አመት ላይ፣ የቴክኒክና ሙያ ተማሪዎች ቁጥር፣ ከሰላሳ እጥፍ በላይ በማደግ ከ350ሺ በላይ ሆኗል።

የ“መሰረተ ልማት” አቅርቦት
በ1947 ዓ.ም፣ በአገሪቱ የነበረው አመታዊ የኤሌክትሪክ ሃይል አቅርቦት፣ 33 ጊጋዋትሃወር እንደነበር የውሃ ሚኒስቴር ባለሙያ መረጃ ያሳያል። በአማካይ ለአንድ ሰው 1600 ዋትአወር... በጣም ትንሽ ነው። ለአንድ ቤተሰብ በቀን ለ25 ደቂቃ አንድ አምፖል ብቻ ያበራ ነበር እንደማለት ነው። እስከ አብዮቱ ዋዜማ ድረስ ሃያ ዓመት ባልሞላ ጊዜ ውስጥ ግን፣ አቅርቦቱ በ18 እጥፍ ጨምሯል። 18 እጥፍ? ፈጣን እድገት ነው።
የአለም ባንክ መረጃ እንደሚያሳየው፣ በአብዮቱ ዋዜማ አመታዊው የኤሌክትሪክ ሃይል አቅርቦት 590 ጊጋዋትአወር ደርሶ ነበር። ግን በእነዚሁ አመታት ውስጥ የሕዝብ ቁጥርም ስለጨመረ፣ የኤሌክትሪክ ሃይል የማግኘት እድል በ18 እጥፍ ሳይሆን በ11 እጥፍ ነው የጨመረው። ይሄም ቀላል አይደለም። በቤተሰብ በየቀኑ 5 ሰዓት ያህል አምፖል እንደማብራት ቁጠሩት። ይሄ በንጉሡ ዘመን ነው።
በደርግ ዘመንስ? በ17 የደርግ አመታት ውስጥ፣ የኤሌክትሪክ ሃይል አቅርቦት 1210 ጊጋዋትአወር ነው የደረሰው። በንጉሡ ዘመን ከነበረው ጋር ሲነፃፀር በአንድ እጥፍ ብቻ ነው የጨመረው። ግን ኢትዮጵያውያን የኤሌክትሪክ ሃይል የማግኘት እድላቸው ብዙም አልጨመረም። ለምን ቢባል፣ የሕዝብ ቁጥርም ጨምሯላ። እናም፣ በቤተሰብ ሲሰላ፣ በየቀኑ 6 ሰዓት ለማይሞላ ጊዜ አንድ አምፖል የማብራት ያህል ነው። በአጭሩ፣ በደርግ ዘመን ኤሌክትሪክ የመጠቀም እድል የተሻሻለው፣ ከሰባት በመቶ ባነሰ መጠን ነው።
በኢህአዴግ ዘመንስ? ከ1983 ዓ.ም እስከ 2003 ዓ.ም ድረስ ያለውን የሃያ አመታት እድገት እንመልከት። የኤሌክትሪክ ሃይል አቅርቦቱ በምን ያህል ጨመረ? አሁንም የአለም ባንክ መረጃን ነው የምጠቅሰው። በጊጋዋትአወር፣ 1210 የነበረው ወደ 5000 ገደማ ጨምሯል። በአራት እጥፍ ገደማ ማለት ነው። ነገር ግን፣ በንጉሡ ዘመን እስከ አብዮቱ ዋዜማ ድረስ በነበሩ ሃያ ዓመታት፣ የኤሌክትሪክ አቅርቦት ከ18 እጥፍ በላይ ማደጉን መዘንጋት የለብንም። በደርግ ዘመን ከነበረው ጋር ሲነፃፀር ግን፣ በኢህአዴግ ዘመን የታየው እድገት በእጅጉ የተሻለ ነው። ሰዎች በኤሌክትሪክ የመጠቀም እድላቸውስ ምን ያህል ተሻሻለ? በኢህአዴግ ሃያ አመታት ውስጥ፣ ከአንድ እጥፍ በላይ ተሻሽሏል። በቤተሰብ ሲሰላ፣ በየቀኑ ወደ 15 ሰዓታት ያህል አንድ አምፖል ለማብራት የሚችል የኤሌክትሪክ ሃይል ተገኝቷል እንደማለት ነው።
እንግዲህ አስቡት። በ1947 ዓ.ም አንድ የኢትዮጵያ ቤተሰብ በአማካይ በየቀኑ ለ25 ደቂቃ ብቻ አንዲት አምፑል ማብራት ይችል ነበር። በ1966 ዓ.ም፣ በየቀኑ ለ5 ሰዓታት ያህል ማብራት ቻለ። በ1983 ዓ.ም ወደ 6 ሰዓት ያህል ፎቀቅ አለ። በ2003 ዓ.ም፣ ወደ 15 ሰዓት ገደማ አደገ። የትኛው ዘመን እድገት ይሻላል?
እንደ ኤሌክትሪክ ሃይል አቅርቦት ሁሉ፤ የመንገድ ግንባታ፣ የአውሮፕላን ትራንስፖርትና የስልክ መስመር አገልግሎትም እንዲሁ፤ ከአብዮቱ ዘመናት ይልቅ በንጉሡ ጊዜ የተሻለ እድገት ተመዝግቧል። ለምሳሌ በቴሌኮሙኒኬሽን ዘርፍ፤ ከ1950 ዓ.ም እስከ 1966 ዓ.ም ድረስ ወደ ስድስት እጥፍ ገደማ በመስፋፋት፣ 45ሺ ገደማ የስልክ መስመሮች አገልግሎት ላይ ውለዋል።
በደርግ ዘመንስ? በሁለት እጥፍ ገደማ ነው ያደገው - ወደ 135ሺ ገደማ የስልክ መስመሮች። እንደ ንጉሡ ዘመን ከስድስት እጥፍ በላይ እድገት የታየው በኢህአዴግ ዘመን ነው። የስልክ መስመሮች ቁጥር በሃያ አመታት ውስጥ 900ሺ ደርሰዋል።
ይህም ብቻ አይደለም። እስከ አብዮቱ ዋዜማ ድረስ፣ የኤክስፖርት ገበያ አራት እጥፍ ገደማ አድጓል - ከ70 ሚሊዮን ዶላር ወደ 270 ሚሊዮን ዶላር። በደርግ ዘመን፣ በእነዚያ ሁሉ አመታት፣ የኤክስፖርት ገበያ በአንድ እጥፍ እንኳ ማደግ አልቻለም። ከ470 ሚሊዮን ዶላር አካባቢ አላለፈም። በኢህአዴግ ዘመንም በመጀመሪያዎቹ አስር አመታት፣ ከኤስፖርት ገበያ የተገኘው ገቢ እዚያው ገደማ ተገድቦ ቆይቷል። ከዚያ በኋላ ነው ከቀድሞው የተሻለ ፈጣን እድገት መታየት የጀመረው። በጥቅሉ፣ በሃያ የኢህአዴግ አመታት ውስጥ እስከ 2003 ዓ.ም ድረስ የኤክስፖርት ገቢ፣ ከአራት እጥፍ በላይ በማደግ፣ ከ2 ቢሊዮን ዶላር በላይ ሆኗል - በንጉሡ ዘመን ከተመዘገበው እድገት ጋር ተቀራራቢ ነው።  

የእህል ምርትና እጦት
የእህል ምርትን ደግሞ እንመልከት። ከአብዮቱ በፊት በነበሩ 20 ዓመታት፣ ለአንድ ሰው በአማካይ በየአመቱ 175 ኪሎ ገደማ እህል ይመረት ነበር። በአብዮቱ ዘመናት በደርግ ጊዜስ? ለአንድ ሰው በአማካይ 135 ኪሎ ገደማ እህል ነው በየዓመቱ ሲመረት የነበረው። በሌላ አነጋገር፤ የሕዝብ ብዛትን ከግምት አስገብተን ስናሰላው የእህል ምርት፣ በንጉሡ ዘመን የ30 በመቶ ብልጫ ነበረው።
በኢህአዴግ ዘመንስ? በመጀመሪያዎቹ የኢህአዴግ አስር አመታት፣ የአገሪቱ የእህል ምርት፣ ከደርግ ዘመንም የባሰ ነበር - በየአመቱ በአማካይ ለአንድ ሰው 125 ኪሎ እህል ነበር የሚመረተው። ቀጥለው ባሉት አስር አመታትስ? ምርቱ በአማካይ ወደ 165 ኪሎ ግራም ገደማ ደርሷል። በእርግጥ ያለፉትን ስምንት አመታት ብቻ ካየን፣ የአገሪቱ የእህል ምርት እየተሻሻለ፣ በአማካይ 175 ኪሎ ገደማ እንደደረሰ እናያለን። በአጠቃላይ ሲታይ፤ ከአብዮቱ ዋዜማ ጀምሮ ወደ ታች ሲያሽቆለቁል የነበረው አብዮታዊ የውድቀት ጉዞ ቀስ በቀስ የተገታው፤ የሶሻሊዝም አብዮት ከተገታ በኋላ ነው። ቀስ በቀስም እያገገመ፣ የአገሪቱ ኢኮኖሚ በንጉሱ ዘመን ወደ ነበረበት ደረጃ ለማደግ ችሏል። በሌላ አነጋገር፤ ኢትዮጵና ኢትዮጵያዊያን በአብዮቱ ሳቢያ ለድህነትና ለረሃብ ከመዳረጋቸው በተጨማሪ፤ ለ30 አመታት ያህል የኋሊት ተጉዘዋል።

  • የብልሹ አሠራርና ሙስናን ችግር በዐደባባይ የተናገሩ የመጀመሪያው ፓትርያርክ ናቸው
  • ፓትርያርኩ ጽኑ አቋም ስለሌላቸው ለጣልቃ ገብነት የተመቹ ኾነዋል
  • ጣልቃ ገብነቶችን መቋቋምና የቅ/ሲኖዶሱን የውሳኔ ልዕልና ማስከበር ይጠበቅባቸዋል
  • ፓትርያርኩ ዙሪያቸውን መፈተሽ አለባቸው
  • ብቃት ያለው የአማካሪ መዋቅር  ያስፈልጋቸዋል

የካቲት 21 ቀን 2005 ዓ.ም ፤ ለስድስተኛው የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ፓትርያርክ ምርጫ ከቀረቡት አምስት ዕጩዎች መካከል በኢየሩሳሌም የኢትዮጵያ ገዳማት ሊቀ ጳጳስ አቡነ ማትያስ በከፍተኛ ድምፅ መመረጣቸው ተነገረ። ሊቀ ጳጳሱ በቤተ ክርስቲያኒቱ የፓትርያርኮች ምርጫ ታሪክ ከፍተኛውን የመራጮች ድምፅ በማግኘት አሸናፊ መኾናቸው በተገለጸበት ወቅት የብዙዎችን ትኩረት በሳበ ኹኔታ በመስቀላቸው ሲያማትቡ ታዩ።
የወቅቱን ስሜታቸውን አስመልክቶ ‹‹ዜና ቤተ ክርስቲያን›› በተሰኘው መጽሔት ለቀረበላቸው ጥያቄ በሰጡት ምላሽ÷ ‹‹ፓትርያርክ እኾናለሁ የሚል መንፈስ በውስጤ ስላልነበረ ውጤቱ ሲገለጽ እንዴት ነው ይህ የእግዚአብሔር ሥራ ምንድን ነው ከሚል ደነገጥኩኝ፤ በዚያው ቅጽበት የተሰማኝ፣ እግዚአብሔር ይህን ታላቅ ሓላፊነት እንዴት እችለዋለሁ? በል አንተ ታውቃለህ፤›› የሚል እንደነበር አስረድተዋል፡፡
ከምርጫው ሦስት ቀናት በኋላ የካቲት 24 ቀን 2005 ዓ.ም በመንበረ ጸባዖት ቅድስት ሥላሴ ካቴድራል በተከናወነው ሥርዐተ ሢመት÷ ለፓትርያርክነት መመረጣቸው የቤተ ክርስቲያኒቱ ጥሪ እንደኾነና ጥሪውን የተቀበሉት መኾኑን፣ መቀበላቸውም ለክብርና ለልዕልና ሳይኾን ለመሥዋዕት በመታዘዝ በመኾኑ የቅዱስ ሲኖዶሱን አባላት በመያዝ በጋራ እንደሚወጡት ያላቸውን እምነት ተናግረው ነበር፡፡
ፓትርያርኩ በዚያ ንግግራቸው ‹‹ቅዱስ ሲኖዶሱ በራሱ መተማመን አለበት›› ሲሉ በአጽንዖት የተናገሩ ሲኾን እንደ አንድ ልብ አሳቢ፣ እንደ አንድ ቃል ተናጋሪ ኾኖ በሥምረት ከሠራ፣ ችግር ይኖራል ብለው እንደማያምኑ ገልጸዋል፡፡ በቅዱስ ሲኖዶሱ ሊሠሩ ይገባል በሚል ካሳወቋቸው ተግባራት መካከልም ቤተ ክርስቲያኒቱ ፍትሕ ርትዕ እኩልነት የሞላባት፣ መልካም አስተዳደር የሰፈነባት፣ የእውነትና የሐቅ መገኛ እንድትኾን በመንፈሳዊነት፣ ታማኝነትና ተጠያቂነት የተደገፈ መጠነ ሰፊ የሥራ እንቅስቃሴ ማድረግን ይጨምራል፡፡ ‹‹እምነትና ሐቅ በቤተ ክርስቲያን ካልተገኙ ከየት ይገኛሉ?›› ሲሉ የጠየቁት ፓትርያርኩ፤ ካህናትና ቤተ ክርስቲያኒቱን በሞያቸውና በልግሥናቸው አቅፈው ደግፈው የያዙ ምእመናንም የድርሻቸውን ለመወጣት ብርቱ ጥረት ማድረግ አለባቸው ማለታቸውም ይታወሳል፡፡
ከፕትርክና ሢመቱም በኋላ ለብዙኃን መገናኛዎች በሰጧቸው ቃለ ምልልሶች÷ ሰው ሊመሰገንም ሊሾምም፣ ሊሻርም፣ ሊወቀስም የሚገባው በጠባዩ፣ በግብረ ገብነቱ፣ በትምህርቱ ብቻ እየተመዘነ እንጂ በዘሩ አንወደውም አንጠላውም በማለት በቤተ ክርስቲያኒቱ አስተዳደር ውስጥ ሥር የሰደደ የመጠቃቀሚያ መንገድ ነው የሚባለውን በጎሰኝነት መሳሳብን ተቃውመዋል፡፡
ቤተ ክርስቲያኒቷ ታላቅ መኾኗንና ለታላቅነቷ የሚመጥኑ ሰዎች መገኘት እንዳለባቸው በአጽንዖት የተናገሩት ፓትርያርኩ፣ ‹‹የተሟላና የተቃና ሥራ ለመሥራት ከኹሉ አስቀድሞ ብቃትና ጥራት ያለው ሥራ መሥራት ያስፈልጋል፡፡ ለዚኽ ደግሞ ሰው በሰው ላይ መደራረብ ሳይኾን ትምህርትና ችሎታ ያለው፣ ለተመደበበት የሥራ ደረጃ የሚመጥን ሰው መቀመጥ አለበት፤›› ብለዋል፡፡
የቤተ ክህነቱ አስተዳደር ከላይ እስከ ታች ተስተካክሎ የመልካም ሥራ አብነት ይኾን ዘንድ ‹‹ሙስና ይጥፋ፤ ተጠያቂነትና ሐቀኝነት ይስፋፋ›› የሚለውን ዐዋጅ ደጋግመው በማሰማት እየታወቁ የመጡት ፓትርያርኩ፤ ቅዱስ ሲኖዶስ የቤተ ክርስቲያኒቱን ስም ለመጠበቅና ክብርዋን ለመመለስ ሊወስዳቸው ይገባል ያሏቸውን የለውጥ ርምጃዎች በመዘርዝር በምልዓተ ጉባኤው አጀንዳነት አስይዘው ለማስወሰን አስችለዋል፡፡
ፓትርያርኩ ሥር ነቀል ለውጥን የሚያመጡና ቆራጥ አቋምን የሚሹ ናቸው ያሏቸው እኒህ ርምጃዎች÷ ብልሹ አሠራር በፀረ-ሙስና እንቅስቃሴ የሚታረምበትና የሚወገድበት፣ የአስተዳደር መዋቅሩና የሚሠራባቸው ደንቦች ሕጎች፣ግልጽነትና ተጠያቂነት እንዲኖረው ተደርጎ የሚሻሻልበት፣ የቤተ ክርስቲያኒቱ ራእይና ተልእኮ በግልጽ የሚታይበት ስትራተጅያዊ የአመራር ሥርዐት የሚነደፍበት፣ ከጠቅላይ ቤተ ክህነት እስከ አጥቢያ ላለው የገንዘብ አያያዝ አንድ ወጥ የኾነ ሥርዐት የሚዘረጋበት እንደኾነ አመልክተዋል፡፡
አቡነ ማትያስ አሳፋሪና አሳዛኝ ነው ያሉት የአሠራር ብልሽት ሳይታረም ቢቀጥል ቤተ ክርስቲያኒቱ ለሚገጥማት አስከፊ ችግር ፓትርያርኩ ራሳቸውን ከተወቃሾች ተርታ በመቁጠር ቤተ ክርስቲያኒቱን የሚታደግና ችግሮቿን የሚቀርፍ አጀንዳ በመያዝ ‹‹በእግዚአብሔር፣ በታሪክና በመጪው ትውልድ ፊት›› የሚመዘን፣ ችግር ፈቺ ውሳኔ እንዲወሰን የቅዱስ ሲኖዶሱን አባላት አነሣስተዋል፡፡
ፓትርያርኩ ከሹመታቸው በኋላ ለመጀመሪያ ጊዜ በርእሰ መንበርነት የመሩትና በግንቦት ወር 2005 ዓ.ም. የተካሔደው የቅ/ሲኖዶስ ምልዓተ ጉባኤ በይፋ ባስታወቁት በዚህ መግለጫቸው ላይ በመወያየት፣ ቤተ ክርስቲያኒቱ ማኅበራዊና መንፈሳዊ ሥራዎቿን በመሪ ዕቅድ በመምራት፣ ሙስናንና የመልካም አስተዳደር ዕጦትን ከሥሩ ለመቅረፍ የሚያስችል ጥናት የሚያቀርብ ከሊቃነ ጳጳሳት፣ ከሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን፣ ከቤተ ክህነቱ የሥራ ሓላፊዎችና ከምሁራን ምእመናን የተውጣጣ ዐቢይ ኮሚቴ ሠይሟል፡፡
ይኸው የቅ/ሲኖዶሱ የምልዓተ ጉባኤ ስብሰባ፣ የቤተ ክርስቲያኒቱ የአደረጃጀትና አሠራር ጥናት የሁሉም አህጉረ ስብከት ማእከልና የመንበረ ፓትርያርኩ መቀመጫ በኾነው በአዲስ አበባ ሀ/ስብከት እንዲደረግ መመሪያ ሰጥቷል፡፡ ሀ/ስብከቱም በመዋቅርና አደረጃጀት፣ በሰው ሀብት አስተዳደር፣ በሒሳብ አሠራርና ቁጥጥር የሚታይበትን የገዘፈና የተመሰቃቀለ ችግሩን ለመፍታት የባለሞያ ቡድን አቋቁሞ በፍጥነት ወደ ተግባር ገብቷል፡፡
በመንበረ ፓትርያርክም በአዲስ አበባ ደረጃም የተቋቋሙት ሁለቱም አካላት የጥናት ውጤታቸውን በጥቅምት ወር 2006 ዓ.ም. ለተካሔደው የቅ/ሲኖዶስ ምልዓተ ጉባኤ አቅርበው በማስገምገም የወሳኝ አካሉን ይኹንታ ከማግኘታቸውም በላይ ቀጣይ የአፈጻጸም አቅጣጫ ተሰጥቷቸዋል፤ የመሪ ዕቅድ ማህቀፉን ያስገመገመው ዐቢይ ኮሚቴ በቀጣይ ዕቅዱን በሥራ መተርጎም በሚያስችል ኹኔታ በዝርዝር አዘጋጅቶ እንዲያቀርብ መመሪያም ተሰጥቶታል፡፡
የአዲስ አበባውን የአደረጃጀትና የአሠራር ለውጥ የሠራው የባለሞያ ቡድንም ጥናቱን ወደ ታች አውርዶ በካህናት፣ በምእመናንና በሰንበት ት/ቤት ወጣቶች በውይይት ካዳበረ በኋላ፣ለቋሚ ሲኖዶስ እንዲያቀርብና በቋሚ ሲኖዶሱ እንዲጸድቅ በምልዓተ ጉባኤው በተሰጠው የአፈጻጸም አቅጣጫ መሠረት ተግባሩን አከናውኖ የብዙኃን ካህናትና ምእመናን ተቀባይነት ያረጋገጠውን የጥናት ሰነድ በሀ/ስብከቱ አማካይነት ለቅ/ሲኖዶሱ አስረክቧል፡፡
ከነገ በስቲያ ሰኞ፣ የካቲት 24 ቀን 2006 ዓ.ም. በሚከበረው አንደኛ ዓመት የበዓለ ሢመት ዋዜማቸው ላይ የሚገኙት ብፁዕ ወቅዱስ ፓትርያርኩ፣ በቀጣዩ የሥራ ዘመናቸው የተናገሯቸውንና ተጠንቶ የቀረበላቸውን በተግባር ለመተርጎም የሚንቀሳቀሱበት እንደሚኾን አዲስ አድማስ ያነጋገራቸው የቤተ ክርስቲያኒቱ ሓላፊዎች፣ አገልጋይ ካህናትና ምእመናን ተስፋቸውን ገልፀዋል።
ቤተ ክህነቱ ያለበትን መሠረታዊ ተልእኮውን የማያገለግል የተንዛዛ ቢሮክራሲ፣ ወገንተኝነትና ሙስና በፓትርያርክ ደረጃ አምነውና ተቀብለው በዐደባባይ ገልጠው ለመናገር አቡነ ማትያስ የመጀመሪያው እንደኾኑ የሚናገሩት አንድ አገልጋይ፤ የፓትርያርኩ መግለጫዎች በየአጥቢያቸው ችግሩን የሚጋፈጡ ወገኖችን በልዩ ልዩ መንገድ እንዳነሣሣ ይህም ቢያንስ ብልሹ አሠራሩን ለሕገ ወጥ ጥቅም ያዋሉ አማሳኞችን እንዳሸማቀቀ ይገልጻሉ፡፡
ለዓመታት የተከማቸው የቤተ ክርስቲያኒቱ ዘርፈ ብዙ ችግር በአንድ ዓመት ተጠንቶ ሊታወቅ ይችል እንደኾነ እንጂ መፍትሔ ያገኛል ተብሎ እንደማይጠበቅ የጠቀሱት አገልጋዩ፤ አንድ ዓመት የፓትርያርኩን ስኬት ለመገምገም በቂ አይደለም ይላሉ፡፡ ፓትርያርኩ በጵጵስና ከተሾሙበት ጊዜ ጀምሮ በውጭ የነበሩ እንደመኾናቸው ቤተ ክህነቱን የመምራት ልምድ ሊያንሳቸው እንደሚችል ጠቁመው ይህን ክፍተት የሚጠቀሙ ከቀድሞም የነበሩና ዛሬም ያልታጠፉ የጥፋት እጆችን ተጽዕኖ በፓትርያርኩ ዙሪያ እንደሚያስተውሉ ገልጸዋል፡፡ ለዚህም ፓትርያርኩ የሚያስጠጓቸውን አማካሪዎች ማንነት በጥንቃቄ መለየት እንደሚኖርባቸው አስተያየታቸውን ሰጥተዋል፡፡
ስለ ፓትርያርኩ የአንድ ዓመት ጉዞ የተጠየቁትና ስማቸው እንዳይገለጽ የፈለጉ በጠቅላይ ቤተ ክህነት ከፍተኛ የሥራ ሓላፊ፣ ፓትርያርኩ ከተሾሙበት ዕለት አንሥቶ ያስተጋቧቸውን የተቋማዊ ለውጥ ዕሴቶችና መርሖዎች ተግባራዊ ለማድረግ ዙሪያቸውን መፈተሽ አለባቸው የሚለውን አስተያየት ይጋራሉ፡፡ ከቅርብ ጊዜ ወዲህ ያለው ኹኔታም ብቃት ያላቸውን እውነተኛ ባለሞያዎች ከፓትርያርኩ የሚያሸሽ እንጂ የሚያቀርብ አይደለም ብለዋል፡፡
የአስተዳደራዊ መዋቅር ማሻሻያ ሒደት የራሱ ተግዳሮቶች እንዳሉት የሚናገሩት የሥራ ሓላፊው፣ የአመራር ብቃትና ብስለት ተግዳሮቶቹን ለበጎ ለውጦ በመጠቀም እንደሚረጋገጥ ያስረዳሉ፡፡ ፓትርያርኩ ሥር ነቀልና ቆራጥ ተግባራዊ ርምጃ እወስዳለኹ ብለው በጀመሩት እንቅስቃሴ ተቃውሞ ሲገጥማቸው፣ ተቃውሞውን የማዳመጥ አባታዊ ሓላፊነት ቢኖርባቸውም ዋናውን የቅ/ሲኖዶሱን ውሳኔ ሳይቀር እስከማመቻመች መድረሳቸው የፀረ ሙስና አቋማቸው ከሚዲያ ፍጆታና ከንግግር ያላለፈ፣ የሚናገሩትንም ያህል ጠንካራና ጽኑ አቋም የሚይዙና ውሳኔ ሰጭ ናቸው ብለው እንዳያምኑ እንዳደረጋቸው አስረድተዋል፡፡ ይህም በውጤቱ የለውጥ ተቃዋሚዎቹን በማፈርጠምና የለውጥ ተስፋውን በማመንመን ሒደቱን አደጋ ውስጥ ሊከተውና የቤተ ክርስቲያኒቱን ችግር የበለጠ ሊያወሳስበው እንደሚችል ስጋታቸውን ገልጸዋል፡፡
ለፓትርያርኩ የአቋም ጽናት፣የሊቃነ ጳጳሳቱ የአቋም አንድነት አስፈላጊ ነው የሚሉት ሌላው አስተያየት ሰጪ፤ ከምንጊዜውም በላይ በቤተ ክህነቱ ላይ ተባብሶ የሚታየውን የተቋማዊ ለውጡን ሒደት የሚያደናቀፉ አላስፈላጊ ጣልቃ ገብነቶችን መቋቋምና የቅ/ሲኖዶሱን የውሳኔ ልዕልና ማስከበር እንደሚገባ ይመክራሉ፡፡
ፓትርያርኩ በተመረጡበት ቀን “እግዚአብሔር ይህን ታላቅ ሓላፊነት እንዴት እችለዋለሁ? በል አንተ ታውቃለህ›› ማለታቸው በርግጥም የሚገባ ነው ያሉት እኚሁ አስተያየት ሰጪ፤ ታላቋንና ጥንታዊቷን ቤተ ክርስትያን በአባትነት ለመምራት ተግዳሮቱ የበዛ ቢሆንም ወደ ዕድገትና ሥልጣኔ የሚያደርሰው ጎዳና በአቡነ ማትያስ ዘመነ ፕትርክና መጠረግና መደልደል ይገባዋል ብለው እንደሚያምኑ ተናግረዋል፡፡


              ዓለም በሁለት ተከፍላ በነበረ ዘመን ማለትም በካፒታሊስትና በሶሻሊስት ጐራ፤ ይወራ የነበረ አንድ ውጋውግ (witticism) አለ፡፡
ድሮ አንድ ጊዜ በፖላንድ አገር ከፍተኛ የሥጋ ዕጥረት ተፈጠረ፡፡ ህዝቡ አማረረ፡፡ ጋዜጦች፣ ሬዲዮ፣ ቴሌቪዥን፣ ወሬው የሥጋ ዕጥረት ነገር ሆነ (ያው እንደኛው አገር)፡፡ ልዩ ልዩ ዓለም አቀፍ ሚዲያዎች እንደልማዳቸው ሰፋፊ ዘገባ ይሰጡበት ጀመር፡፡ (ያው በእኛ ላይ እንደሚያደርጉት)
ይህን የተገነዘበ አንድ ኩባንያ “ዓለም-አቀፍ የጥያቄና መልስ ውድድር” አዘጋጅቶ “በጣም ከባድ ከባድ ሽልማት ስለምሰጥ የቻለ ይወዳደር”፤ ብሎ አዋጅ አወጣ፡፡
በአዕምሮአችን እንተማመናለን ያሉ አዋቂዎች በሺዎች ተመዘገቡ፡፡ የማጣሪያ ውድድሮች ተካሄዱ፡፡ ጉዳዩ ስለ ፖላንድ የኢኮኖሚ ችግር ነው፡፡ ለመጨረሻ ፍልሚያ የደረሱት ፋይናሊስቶች ሶስት ናቸው፡፡ የአሜሪካ፣ የህንድና የሩሲያ ተፎካካሪዎች፡፡
ለመጀመሪያው ተረኛ የቀረበለት ጥያቄ
“Why is there a shortage of meat in Poland?” የሚል ነው፡፡ “በፖላንድ የሥጋ ዕጥረት ለምን መጣ?” ነው፡፡
በመጀመሪያ የአሜሪካዊው ተራ ነበረ፡፡ እሱም፤ አሰበ አሰበና፣ “What is Shortage?” አለ፡፡ ዕጥረት ማለት ምን ማለት ነው? (እንግዲህ “ዕጥረት” ማለት ቃሉም እራሱ በእኔ አገር አይታወቅም ማለቱ ነው፡፡)
ሁለተኛው የህንዱ ተራ ሆነ፡፡ ሌላ ጥያቄ ይጠይቁኛል ብሎ ሲጠብቅ ያው ጥያቄ ቀረበለት
“why is there a shortage of meat in poland” “በፖላንድ የሥጋ ዕጥረት ለምን መጣ? ህዳንዊውም፤ ትንሽ አሰበና፤ “what is meat?”
“ሥጋ ማለት ምን ማለት ነው?” አለ፡፡ (በህንድ አገር ሥጋ ከማይበሉት ወገን ነው ማለት ነው ህንዱ)
በመጨረሻ፤ ተራው የሩሲያዊው ሆነ፡፡ እሱም ሌላ ጥያቄ ይጠይቁኛል ብሎ ሲጠብቅ፤
“why is there a shortage of meat in Poland?” ሆነ ጥያቄው፡፡ “በፖላንድ ለምን የሥጋ ዕጥረት መጣ?”
ሩሲያዊውም አስቦ አስቦ፤ አስራሚ ጥያቄ አመጣ፡-
What is “why?” ሲል ጠየቀ፡፡
“ለምን?” ብሎ ጥያቄ ራሱ፤ ምን ማለት ነው ማለቱ ነው! (ያኔ በሩሲያ “ለምን?” ብሎ መጠየቅ የማይሞከር ነገር ነው፡፡)
*             *                    *
“ለምን?” ብሎ የማይጠይቅ ህብረተሰብ ተስፋ የለውም፡፡ “ለምን?” ተብሎ መጠየቅን የማይፈልግ መንግስትም ተስፋ የለውም፡፡ ሌሎች ብዙ ተጨማሪ ነገሮች ቢኖሩበትም የሩሲያ መንግስት መንኮታኮት ዕጣ-ፈንታው የሆነበት ምክንያት “ለምን?” መባል አለመፈለጉ፤ ኢ-ዲሞክራሲያዊነቱ፣ ሀሳባችሁን አትግለፁ ማለቱ፣ ህዝቡ ቃሉ እስኪጠፋው ድረስ “ለምን?” በማለት መገደቡ ነው፡፡ ለምን ብለን እንጠይቅ፡፡
ነዳጅ ይጠፋል! ለምን? መብራት ይጠፋል! ለምን?፤ ስልክ ይሰወራል! ለምን?፤ ውሃ ይደርቃል! ለምን … የባንክ ሲስተም የለም ይባላል-ለምን? ብዙ ለምኖች አሉ፡፡ ግን ጠያቂ የለም ተጠያቂም የለምም፡፡ ለምን? ለምን ብዙ? ነው፡፡... የሚታሸጉ ቤቶች አሉ፡፡ አንዳንድ ቤቶችን እየዘለሉ ይታሸጋሉ፡፡ ዝላዩ ለምን መጣ?... ዛሬ ለምን ብሎ መጠየቅ ያልቻለው ህዝብ ለምኖቹን ማጠራቀሙ አይቀርም፡፡ ከለምን ወደ ለምንም አልመለስም እንዳይሸጋር ማሰብ ያስፈልጋል፡፡ እኛ ትልቅ ነገር እየሰራን ሊሆን ይችላል፡፡ ወደ ትላልቆቹ ተግባሮች የሚመጡትን ቀጫጭን ቧንቧዎች ቆሻሻ ከዘጋቸው ትልቁ ቧንቧ የት ይደርሳል?
በሀገራችን እንደሰንሰለታሙ ተራራ፤ ሰንሰለታማ ሙስና መኖሩን እየሰማን ነው (network of corruption መሆኑ ነው) እንደዋዛ የሚዘረጋ አይደለም-በአገራዊ መስክ ስናስበው፡፡ ይህ አይነኬ (insulated) ሰዎች መኖራቸውን ነው የሚናገረው:: ወይም ብረት-ለበስ ናቸው ማለት ነው:: ጥይት-ከላ (Bullet-proof) አካል የታደሉ፡፡ አንድ የፖለቲካ አቋሙን የቀየረ ፖለቲከኛን አንድ አድናቂው፤ “ብርሃኑን በማየትህ ተደስቻለሁ” አለው “አዬ ወዳጄ እኔ ብርሃኑን አላየሁም ይልቅስ ቃጠሎው፣ ቃጠሎው ነው የባሰብኝ!” አለ ይባላል፡፡ በሙስና ረገድ ቃጠሎው ገና የመጣ አይመስልም፡፡ በፓርቲ ቃጠሎ ገና ይፋ ያልሆነ ተቃጣይ ብዙ አለ፡፡ ሙስና የማያደርሰን ቦታ የለም! የናይጄሪያን ሙስና ጉድ ጉድ ስንል እኛው ሃዲድ እየሰራን ነው! “ጮሃ የማታውቅ ወፍ እለፉ እለፉ ትላለች!” ሆኗል! ኧረ ለምን እንበል!
ኢትዮጵያ ውስጥ ብዙ የዓለም-አቀፍ ቀኖች ማክበር ወደ ፋሽንነት እየተቀየረ ይመስላል፡፡ የግሎባላይዜሽኑ በዓላዊ ገፅታ ካልሆነ በስተቀር ነው እንግዲህ፡፡ ቢቀናን “የጉዳይ-አስፈፃሚዎች ቀን” ብናከብር ለእኛ አግባብነት ሳይኖረው አይቀርም፡፡ ጉደኛ አገር ሆነናል እኮ፡፡ “ምን ትሰራለህ?” ሲባል ጉዳይ አስፈጽማለሁ ይላል አንድ ባለሙያ፡፡ የተማርከውስ አካውንቲንግ፣ ምህንድስና፣ ታሪክ፣ ማኔጅመንት ወዘተ ሲባል፤ “እሱን እንኳ በትርፍ ጊዜዬ እሰራዋለሁ” ይላል፡፡ ኢትዮጵያ ግን ይሄን ያህል የተማረ ዜጋ አለኝ ብላ ለዓለም ባንክ አስመዝግባለች፡፡ እሷም በትርፍ ጊዜዋ ካልሆነ!! ሰሞኑን “የአፍ መፍቻ ቀን” ተከብሯል፡፡ ለብዙ ዓመት የኢንፎርሜሽን ቀንም አክብረናል፡፡ ብዙ የነፃነት ቀኖችንም አክብረናል፡፡ የጀግንነት ቀናት ብዙ አሉን፡፡ የአድዋ ዋዜማ፣ የህውሃት ምስረታ ቀን አለ (የካቲት 11 እና የካቲት 23፤ የከተማ ልጆች ከአድዋ ወደ አድዋ እንዲሉ) ብዙ የፆም ቀኖችንም እናከብራለን፡፡  ዓለም-አቀፍ የጾም መያዣ ቀን ቢኖር ይገላግለን ይሆን? የኤች አይ ቪ ዓለም-አቀፍ ቀን አለ፡፡ የፍትህ ቀን አለ፡፡  የ ---- ቀን፣ የ ---- ቀን፣ የ----ቀን ብዙ ቀን አለን፡፡ (ተስፋዬ ካሳ የተባለው ኮሜዲያን .. “ኧረ ማታውን እንኳን ልቀቁልን” ብሎ ቀልዶ ነበር) እንደቀኖቹ ምክንያትና ብዛት .. ምነው ብዙ ደስታ በኖረን፣ ምነው ብዙ ተግባር በኖረን … ምነው ብዙ ፍቅር በኖረን! ግን የለንም፡፡ አንዳንዴ እንደኛ በኢኮኖሚ የደቀቁ አገሮች ቀኖቹን በውል ለማጣጣም ይችሉ ይሆን ያሰኛል? በባዶ ሆድ የእገሌ ቀን፣ የእንትን በዓል .. ምን ስሜት ይሰጣል? የሚል ብርቱ ጥያቄ ያስነሳል፡፡ ይሄንንም ለምን? ብለን እንጠይቅ፡፡ ትላንትም ዛሬም ምንም ዓይነት ስም እንስጣቸው፤
ሁኔታዎች በከፉ ቁጥር ትኩረት ሳንሰጣቸው ይገዝፉና አልነቃነቅ የሚሉ ይሆናሉ፡፡ ግምገማም፤ አዋጅም፣ ማስፈራራትም፣ ማፈራራትም፣ ካገር ማስወጣትም የማይበግራቸው ደረጃ፤ አይቀሬው ነገር ወደድንም ጠላንም ፈጦ ይመጣል - “መገነዣው ክር ከተራሰ፣ መቃብሩ ከተማሰ “እንደሚለው ነው አበሻ! ከወዲሁ አመጣጡን፣ ከወዲሁ አወጣጡን፣ ከወዲሁ ክፋቱን፣ ከወዲሁ ዐይነ-ውሃውን ስናየው ውጤቱ፤ አንድ የምናውቀው ፊልም እየመሰለን መጥቷል - አጨራረሱ የሚታወቅ!
“አለ አንዳንድ ነገር፣
አለ አንዳንድ ነገር
በዚህ ቢሉት በዚያ፣ ከመሆን የማይቀር”… ብለው ነበር ከበደ ሚካኤል፡፡
“መላጣ አናት ላይ ጠብ ያለች ውሃ እስካፍንጫ ለመውረድ ምን ያግዳታል?!” የሚለው የወላይታ ተረት መንፈሱ ይሄው ነው! ከዚህ ይሰውረን ጎበዝ!         

        የኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌደሬሽን ለፕሪሚዬር ሊግ ክለቦች ከ17 ዓመት በታች የታዳጊ ውድድር ከሳምንት በኋላ ይጀምራል፡፡ የታዳጊዎችን ውድድርን በጥራት ለመምራት ከፍተኛ ትኩረት የሰጠው የእግር ኳስ ፌዴሬሽኑ በውድድሩ ተሳታፊ በሚሆኑ ክለቦች ላይ አስፈላጊውን  የእድሜ ማጣራት በማከናወን ከሞላ ጎደል ዝግጅቱን እንዳጠናቀቀ  ለማወቅ ተችሏል፡፡ በውድድሩ ከ17 ዓመት በታች ቡድናቸውን የሚያሳትፉ የፕሪሚዬር ሊግ ክለቦች ለተጨዋቾቻቸው የተዘጋጀውን የእድሜ ማረጋገጫ ምርመራ በኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌደሬሽን የህክምና ኮሚቴ የግምባር ፍተሻ እና በቴክኒክ ኮሚቴው ተጨማሪ ማረጋገጫ መሰረት አከናውነዋል፡፡  ከ17 ዓመት በታች የታዳጊዎች ውድድሩ የካቲት 22 እንደሚጀመር የገለፀው የኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌደሬሽን ተሳታፊ ክለቦች አስፈላጊውን ዝግጅት እንዲያደርጉ ጥሪ ያስተላለፈ ሲሆን ዘንድሮ ተሳታፊ የሆኑ ክለቦች ብዛት 9 እንደሆኑና ውድድድራቸውን በደቡብ እና በማዕከላዊ ዞኖች በመከፋፈል እንደሚያደርጉ አስታውቋል፡፡ በማዕከላዊ ዞን  ቅዱስ ጊዮርጊስ፤ ኢትዮጵያ ቡና፤ ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ፤ ደደቢት፤ መብራት ሃይልና ሙገር ሲምንቶ ሲመደቡ፤ በደቡብ ዞን ደግሞ አርባምንጭ ፤ ሲዳማ ቡና እና ሃዋሳ ከነማ ይገኛሉ፡፡
ከ17 ዓመት በታች ውድድሩ የተዘጋጀው በታዳጊዎች ላይ በመስራት የአገሪቱን እግር ኳስ እድገት በጠንካራ መሰረት ላይ ለመጣል ያስችላል ተብሎ ነው የእግር ኳስ ፌደሬሽኑ ለውድድሩ ከፍተኛ ትኩረት በመስጠት ተተኪ ተጨዋቾችን ለብሄራዊ ቡድን ለማፍራት እንደሚንቀሳቀስ  ስፖርት አድማስ ያነጋገራቸው የእግር ኳስ ፌዴሬሽኑ የውድድር ዋና ስራ ሂደት ሃላፊ አቶ ተድላ ዳኛቸው ተናግረዋል፡፡ በኢትዮጵያ እግር ኳስ  የታዳጊዎችን ውድድር ለማካሄድ በፌደሬሽን በኩል እንቅስቃሴው ከተጀመረ ቢቆይም ተግባራዊነቱ አልተሳካም ነበር፡፡ በቀድሞ የፌደሬሽን ስራ አስፈፃሚ የሴቶች እግር ኳስ  ቡድኖችን ከማቋቋም ባሻገር የፕሪሚዬር ሊግ ክለቦች የታዳጊ ቡድኖች እንዲኖራቸውና ውድድር እንዲያካሂዱ ከስምምነት ላይ ተደርሶ እንደነበር ያስታወሱት አቶ ተድላ ዳኛቸው፤ አሁን ያለው አዲስ የስራ አስፈፃሚ ኮሚቴም በወጣቶች ላይ መስራት ለእግር ኳሱ እድገት ወሳኝ አቅጣጫ ነው በማለት የታዳጊዎች ውድድሩን ተግባራዊ ለማድረግ መወሰኑን ይገልፃሉ፡፡
የእድሜ ማረጋገጫ ምርመራዎች
አንድ ክለብ የሀ 17 ቡድን ሲመሰርት ማሟላት ያለበት መስፈርቶች በእግር ኳስ ፌደሬሽኑ በኩል ተቀምጠዋል፡፡ የመጀመርያው የተጨዋቾች የእድሜ ገደብን ማሟላትና ማረጋገጥ ነው፡፡ ይህ ደግሞ ክለቦች በዘመናዊ የህክምና ምርመራ በማከናወን በሚያቀርቡት ማስረጃ ብቻ ሳይሆን በፌዴሬሽኑ የህክምና ኮሚቴ በኩል በግምባር የተጨዋቾችን ተክለሰውነት በተለያዩ ዘዴዎች በመፈተሽ በሚካሄድ  ምርመራ  መረጋገጥ ይኖርበታል፡፡ አቶ ተድላ ዳኛቸው እንደሚያስረዱት ክለቦች በየትኛውም ዘመናዊ የህክምና ተቋም የኤምአርአይ ምርመራቸውን ካከናወኑ በኋላ የፌደሬሽኑ  የቴክኒክ እና የህክምና ኮሚቴዎችን ተጨማሪ ማረጋገጫ ማድረግ ነበረባቸው፡፡ እንደ አቶ ተድላ ዳኛቸው ገለፃ ከኤምአርአይ ምርመራው ሌላ ኮሚቴዎቹ  በተለያዩ መንገዶች የተጨዋቾችን እድሜ ለማጣራት የሰሩት አንዳንድ የማጭበርበር ሁኔታዎችን ለማስቀረትነው፡፡ በዚህም መሰረት የህክምና ኮሚቴው የእያንዳንዱን ክለብ ተጨዋቾች  ወደ ስታድዬም ጠርቶ በአጠቃላይ ተክለሰውነታቸውን ገምግሟል፡፡ ማንኛውም ተጨዋች በሁሉም  ምርመራዎች የእድሜው ትክክለኛነት ካላረጋገጠ መጫወት አይችልም፡፡ ከ17 ዓመት በታች በተዘጋጀው የታዳጊዎች ውድድር ላይ የሚሳተፉ ክለቦች በስብስባቸው የሚይዟቸው ተጨዋቾች እድሜያቸው 15 እና 16 ዓመት  መሆን ሲገባው ይህን የእድሜ ገደብ በሟሟላት እስከ 25 ተጨዋቾች ያስመዘግባሉ፡፡  ክለቦች ውድድሩ ከመጀመሩ በፊት የያዟቸውን ተጨዋቾች እድሜ በሁሉም ምርመራዎች እንዲያረጋግጡ በቂ ጊዜ ተሰጥቷቸው ነበር፡፡ እስከ የካቲት 15  የተሰጠው ቀነ ገደብ ዛሬ ያልቃል፡፡ ከዛሬ በፊት ብዙዎቹ ክለቦች የምርመራ ሂደቱን እንዳጠናቀቁ የሚናገሩት አቶ ተድላ፤ አንዳንድ ክለቦች ቢዘገዩም  በአስቸኳይ አስፈላጊውን መመርያ ተከትለው እንዲሰሩ በማበረታት ውድድሩ ከመጀመሩ በፊት የማጣራት ሂደቱን እንዲጨርሱ ጥረት እያደረግን ነው ብለዋል፡፡ በማዕከላዊ ዞን ካሉት ክለቦች ቅዱስ ጊዮርጊስ፤ ደደቢት፤ መከላከያ፤ ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ሁሉንም መስፈርቶች በሟሟላት እና በማረጋገጥ  የውድድሩን መጀመር በመጠባበቅ ላይ ናቸው፡፡ አርባምንጭ ከነማ እና ሃዋሳ ከነማ ግን ትንሽ ቢዘገዩም በቀጣይ ሳምንት የምርመራውን ሂደት እንደሚጨርሱ ተስፋ ተደርጓል፡፡
የእግር ኳስ ፌደሬሽኑ ከምንጊዜውም በላይ በኢትዮጵያ እግር ኳስ ያለውን የእድሜ ማጭበርበር ችግር ለመፍታት ቁርጠኛ አቋም መያዙን የገለፁት የውድድር ዋና የስራ ሂደት ሃላፊ አቶ ተድላ ዳኛቸው፤ የተጨዋቾች መረጃ  በትክክለኛ መንገድ  ተሰርቶ በዘመናዊ የመረጃ ክምችት  መቀመጥ  ስላለበት የምርመራ ሂደቶችን በትኩረት መከናወናቸውን ያስረዳሉ፡፡ ከታዳጊዎች ውድድሩ ጋር በተያያዘ የተጨዋቾች ምዝገባ የተከናወነው አለም አቀፍ መመርያን በመከተል ነው፡፡ በዚህ መሰረትም በእግር ኳስ ፌደሬሽኑ አሰራር በትክክለኛ ምርመራዎች እድሜው ተረጋግጦ የተመዘገበ ተጨዋች ወደፊት እድሜውን ሊጨምር ወይንም ሊቀንስ የማይቻልበት ሁኔታ ተፈጥሯል፡፡
የውድድሩ አካሄድ እና ጠቀሜታዎች
ከ17 ዓመት በታች የሚካሄደው የታዳጊዎች ውድድር በአንድ ዙር እንደሚደረግ የተናገሩት የውድድር ዋና የስራ ሂደት ሃላፊው፤ የየክለቦቹ ተጨዋቾች ተማሪዎች እንደመሆናቸው ከውድድሩ በተያያዘ ትምህርታቸውን እንዳያስተጓጉልባቸው በሳምንት አንዴ ጨዋታዎችን ለማካሄድ እንደተወሰነና ታዳጊዎቹ በየስታድዬሞቹ በቂ ተመልካች እንዲያገኙ  ከተለያዩ የፕሪሚዬር ሊግና ሌሎች ውድድሮች ጋር ጎን ለጎን በማካሄድ  የፉክክር መንፈሱን ለማሟሟቅ መታሰቡን ገልፀዋል፡፡ በታዳጊዎች ውድድሩ ለሚያሸንፍ ክለብ ልዩ ዋንጫ መዘጋጀቱ እንደማይቀር የጠቀሱት የውድድር ዋና የስራ ሂደት ሃላፊ አቶ ተድላ ዳኛቸው፤ በታዳጊ ደረጃ የሚደረግ ውድድርን በተለያየ የማበረታቻ ድጋፎች ማስኬድ መሰረታዊ ጥቅም ስለሚኖረው የእግር ኳስ ፌደሬሽኑ ስራ አስፈፃሚ በዚህ ረገድ ትኩረት እንደሚሰጥ አስባለሁ ብለዋል፡፡
የፕሪሚዬር ሊግ ክለቦች በታዳጊዎች ውድድር በመሳተፋቸው በርካታ ጥቅሞችን እንደሚያገኙ የውድድር ዋና የስራ ሂደት ሃላፊው ያስገነዝባሉ፡፡ የመጀመርያው  ጥቅም ውድድሩ ለዋና ቡድናቸው በቂ እና ብቁ ተተኪ ተጨዋቾችን የሚያሳድጉበት እድል ለክለቦች ይፈጠርላቸዋል፡፡ ዋና ቡድናቸውን ለማጠናከር ብቻ ሳይሆን ክለቦች በተጨዋቾች የዝውውር ገበያ ከፍተኛ ወጪ የሚያወጡበትንም ሁኔታ የሚያስቀርና ከራሳቸው አልፎ ለሌሎች ክለቦች ወጣት ተጨዋቾችን በዝውውር ገበያ በማቅረብ ገቢ ሊያገኙበት ይችላሉ፡፡ ከክለቦች ተጠቃሚነት ባሻገር ከፍተኛው ውጤት ክለቦች ለብሄራዊ ቡድን ወጣት እና ተተኪ ተጨዋቾችን በየጊዜው እንዲያፈሩ የሚያስችል መሆኑ ነው፡፡  በ2015 እኤአ ኒጀር ላይ በሚደረገው የአፍሪካ የሀ-17 ሻምፒዮና ኢትዮጵያ እንደምትሳተፍ አያይዘው ያነሱት አቶ ተድላ ዳኛቸው፤  በዚህ አህጉራዊ ሻምፒዮና ለሚሳተፈው የኢትዮጵያ ሀ 17 ብሄራዊ ቡድን የሚበቁ ተጨዋቾችን ለማግኘት ውድድሩ አመቺ መድረክ ይሆናል ብለዋል፡፡
በውድድሩ  ክለቦች በዋናነት በስልጠና ወጥ አሰራር እንዲኖራቸው ይደረጋል ያሉት  አቶ ተድላ ዳኛቸው፤  በየክለቡ ታዳጊዎችን የሚያሰለጥኑ አሰልጣኞች ብቃታቸው እንደሚመዘን ወጥ የሆነ የስልጠና መመርያ ተከትለው እንዲሰሩ እና እንዲወዳደሩ ጥረት እንደሚደረግ አስገንዝበው፤ ለዚህም  የኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌደሬሽን የቴክኒክ ዲፓርትመንት የስልጠና ማንዋል በመስራትና አሰልጣኞች ብቃታቸውን የሚያሳድጉባቸው ሴሚናሮች በማዘጋጀት እንደሚንቀሳቀስ በመግለፅም ታዳጊዎች  በወጥ  የስልጠና ሂደት በማለፍ ለብሄራዊ ቡድን ደረጃ ሲደርሱ በተመሳሳይ ብቃት እና አቋም እንዲኖራቸው ያስችላል ብለዋል፡፡
በክለቦች ህጋዊነት ሰርተፍኬት ያለው ወቅታዊ ሁኔታ
ከ17 ዓመት በታች በሚደረገው የታዳጊዎች ውድድር ላይ ክለቦች ቡድኖችን በማቋቋም መሳተፋቸው በአፍሪካ እግር ኳስ ኮንፌደሬሽንን የሚጠየቀውን የአንድ እግር ኳስ ክለብ መመዘኛ ለሟሟላት ወሳኝ መሆኑን የሚገልፁት የውድድር ዋና የስራ ሂደት ሃላፊ አቶ ተድላ ዳኛቸው፤  የክለቦች ህጋዊነት ሰርተፍኬትን በየደረጃው በማግኘት በአህጉራዊ ውድድሮች ለመሳተፍ የሚያስችላቸውን ሁኔታ የሚፈጥር መሆኑን  ያስረዳሉ፡፡ በአፍሪካ እግር ኳስ ኮንፌደሬሽን በወጣ መመርያ መሰረት አንድ ክለብ በውድድር ሲሳተፍ ሊያሟላቸው የሚገቡ መስፈርቶች አሉ፡፡ እነዚህን መስፈርቶች የአፍሪካ እግር ኳስ ፌደሬሽን ያወጣው ያለምክንያት አይደለም፡፡ በሚያዘጋጃቸው አህጉራዊ ውድድሮች ለክለቦች የመሳተፍ ፍቃድ የሚሰጠው ተገቢውን መስፈርት አሟልተው የክለቦች ህጋዊነት ሰርተፍኬት ያገኙትን ብቻ  ነው፡፡  ክለቦች ይሄው የአፍሪካ እግር ኳስ ኮንፌደሬሽን መመርያ ተገልጾላቸው የተቀመጡትን መመዘኛ መስፈርቶች እንዲያሟሉ ከተነገራቸው ሶስተ ዓመታት አልፈዋል፡፡ ከመስፈርቶቹ መካከል በቅድሚያ ክለቦች በአደረጃጀታቸው በወጣቶች ላይ የተመሰረት መዋቅር  እንዲኖራቸው ያስፈልጋል፤ ይህም የእግር ኳሱን ወጥ እድገት ለመቀጠል ወሳኝ ስለሆነ ነው፡፡
ክለቦች በታዳጊዎች እና በወጣቶች ስልጠና ሊያሰሯቸው የሚችሏቸው ብቁ አሰልጣኞች እንዲኖሯቸው ይጠየቃል፡፡ አንድ በፕሪሚዬር ሊግ ደረጃ ተወዳዳሪ የሆነ ክለብ ክለብ የተሟላ ዕህፈት ቤት፤ በቂ የፋይናንሻል አቅም ፤ የስፖርት ማዘውተርያ ስፍራ፤ የተሟላ የባለሙያዎች አደረጃጀት ሊኖረው ይገባል፡፡ በእነዚህ መስፈርቶች መሰረት ክለቦች  በሶስት  ደረጃዎች በኤ፤ ቢ እና ሲ በመመዘን የህጋዊነት ሰርተፍኬት ይሰጣቸዋል፡፡ የህጋዊነት ሰርተፍኬቱን ለመስጠት የእግር ኳስ ፌደሬሽኑ የክለቦች አደረጃጀት፤ አቅም አቅም በግንባር እንዲገመግም ሃላፊነት እንደተሰጠው አቶ ተድላ ዳኛቸው ሲናገሩ፤ ለዚህም ተብሎ ሁለት ኮሚቴዎች ተቋቁመው ከአዲሱ ስራ አስፈፃሚ ኮሚቴ ጋር በመተዋወቅ በቅርቡ ስራቸውን ይጀምራሉ ብለዋል፡፡ በክለቦች ህጋዊነት ሰርተፍኬት አሰጣጥ ላይ የሚሰሩት ኮሚቴዎች አንደኛው ቅደመ ውሳኔ የሚሰጥ ሲሆን ሌላኛው የይግባኝ ሰሚ  ነው፡፡ ቅድመ ውሳኔ የሚሰጠው ኮሚቴ በመጀመርያ ውሳኔ ሰጭነቱ ክለቡ ምን አሟልታል በሚል በቂ ግምገማ እና ክትትል በማድረግ የየክለቡን የፍቃድ ደረጃ የሚወስን ይሆናል፡፡ የይግባኝ ሰሚ ኮሚቴው ደግሞ ክለቦች በቅድመ ውሳኔ ሰጪ ኮሚቴው በተሰጣቸው  ደረጃ ላይ ቅሬታ ካላቸው ይግባኝ ብለው የተሰጣቸውን ምዘና ሊያስተካክሉ የሚችሉበት ነው፡፡
አንዳንድ ሁኔታዎችን በመገንዘብ ለመረዳት እንደሚቻለው በክለቦች ህጋዊነት ሰርተፍኬት መመዘኛ ብዙዎቹ  የኢትዮጵያ ክለቦች በሲ ደረጃ ሲሆኑ በቢ ደረጃ ያሉ ጥቂት ናቸው፡፡ በአሁኑ ወቅት በአገሪቱ እግር ኳስ በኤ ደረጃ ሰርተፍኬት የሚያገኝ ክለብ የለም፡፡ በክለቦች ህጋዊነት ሰርተፍኬት እንዲሰጥ መመርያ ያስፈለገው አንድ ክለብ በአህጉራዊ ደረጃ በሚደረጉ ውድድሮች ለመሳተፍ ማሟሟላት  የሚገባው ደረጃዎች ስላሉ ነው፡፡ ክለቦች በዚህ መመርያ መሰረት ሊያሟሉ የሚገባቸውን መስፈርቶች እንዲያሟሉ በፊፋ በኩል የአቅም ግንባታ ስልጠናዎች በተደጋጋሚ ቢሰጡም ብዙም እየተራመዱ አይደለም፡፡  የፐሪሚዬር ሊግ  ክለቦች አስቀድመው የሴቶች ቡድን በማቋቋም ተንቀሳቀሰው አሁን ውድድር እየተደረገ ውጤቱን በማየት ላይ ናቸው፡፡ ከቅርብ ጊዜ ወዲህ ደግሞ የሀ 17 ቡድኖች መያዛቸው አንዱ ርምጃ ሲሆን አንዳንድ ክለቦች የቴክኒክ ዲያሬክተር መቅጠራቸው፤ በማርኬቲንግ ባለሙያ መስራትም መጀመራቸውም እንደለውጥ የሚታይ ቢሆንም ገና ብዙ መስራት ይጠበቅባቸዋል፡፡

        የኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌደሬሽን ለፕሪሚዬር ሊግ ክለቦች ከ17 ዓመት በታች የታዳጊ ውድድር ከሳምንት በኋላ ይጀምራል፡፡ የታዳጊዎችን ውድድርን በጥራት ለመምራት ከፍተኛ ትኩረት የሰጠው የእግር ኳስ ፌዴሬሽኑ በውድድሩ ተሳታፊ በሚሆኑ ክለቦች ላይ አስፈላጊውን  የእድሜ ማጣራት በማከናወን ከሞላ ጎደል ዝግጅቱን እንዳጠናቀቀ  ለማወቅ ተችሏል፡፡ በውድድሩ ከ17 ዓመት በታች ቡድናቸውን የሚያሳትፉ የፕሪሚዬር ሊግ ክለቦች ለተጨዋቾቻቸው የተዘጋጀውን የእድሜ ማረጋገጫ ምርመራ በኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌደሬሽን የህክምና ኮሚቴ የግምባር ፍተሻ እና በቴክኒክ ኮሚቴው ተጨማሪ ማረጋገጫ መሰረት አከናውነዋል፡፡  ከ17 ዓመት በታች የታዳጊዎች ውድድሩ የካቲት 22 እንደሚጀመር የገለፀው የኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌደሬሽን ተሳታፊ ክለቦች አስፈላጊውን ዝግጅት እንዲያደርጉ ጥሪ ያስተላለፈ ሲሆን ዘንድሮ ተሳታፊ የሆኑ ክለቦች ብዛት 9 እንደሆኑና ውድድድራቸውን በደቡብ እና በማዕከላዊ ዞኖች በመከፋፈል እንደሚያደርጉ አስታውቋል፡፡ በማዕከላዊ ዞን  ቅዱስ ጊዮርጊስ፤ ኢትዮጵያ ቡና፤ ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ፤ ደደቢት፤ መብራት ሃይልና ሙገር ሲምንቶ ሲመደቡ፤ በደቡብ ዞን ደግሞ አርባምንጭ ፤ ሲዳማ ቡና እና ሃዋሳ ከነማ ይገኛሉ፡፡
ከ17 ዓመት በታች ውድድሩ የተዘጋጀው በታዳጊዎች ላይ በመስራት የአገሪቱን እግር ኳስ እድገት በጠንካራ መሰረት ላይ ለመጣል ያስችላል ተብሎ ነው የእግር ኳስ ፌደሬሽኑ ለውድድሩ ከፍተኛ ትኩረት በመስጠት ተተኪ ተጨዋቾችን ለብሄራዊ ቡድን ለማፍራት እንደሚንቀሳቀስ  ስፖርት አድማስ ያነጋገራቸው የእግር ኳስ ፌዴሬሽኑ የውድድር ዋና ስራ ሂደት ሃላፊ አቶ ተድላ ዳኛቸው ተናግረዋል፡፡ በኢትዮጵያ እግር ኳስ  የታዳጊዎችን ውድድር ለማካሄድ በፌደሬሽን በኩል እንቅስቃሴው ከተጀመረ ቢቆይም ተግባራዊነቱ አልተሳካም ነበር፡፡ በቀድሞ የፌደሬሽን ስራ አስፈፃሚ የሴቶች እግር ኳስ  ቡድኖችን ከማቋቋም ባሻገር የፕሪሚዬር ሊግ ክለቦች የታዳጊ ቡድኖች እንዲኖራቸውና ውድድር እንዲያካሂዱ ከስምምነት ላይ ተደርሶ እንደነበር ያስታወሱት አቶ ተድላ ዳኛቸው፤ አሁን ያለው አዲስ የስራ አስፈፃሚ ኮሚቴም በወጣቶች ላይ መስራት ለእግር ኳሱ እድገት ወሳኝ አቅጣጫ ነው በማለት የታዳጊዎች ውድድሩን ተግባራዊ ለማድረግ መወሰኑን ይገልፃሉ፡፡
የእድሜ ማረጋገጫ ምርመራዎች
አንድ ክለብ የሀ 17 ቡድን ሲመሰርት ማሟላት ያለበት መስፈርቶች በእግር ኳስ ፌደሬሽኑ በኩል ተቀምጠዋል፡፡ የመጀመርያው የተጨዋቾች የእድሜ ገደብን ማሟላትና ማረጋገጥ ነው፡፡ ይህ ደግሞ ክለቦች በዘመናዊ የህክምና ምርመራ በማከናወን በሚያቀርቡት ማስረጃ ብቻ ሳይሆን በፌዴሬሽኑ የህክምና ኮሚቴ በኩል በግምባር የተጨዋቾችን ተክለሰውነት በተለያዩ ዘዴዎች በመፈተሽ በሚካሄድ  ምርመራ  መረጋገጥ ይኖርበታል፡፡ አቶ ተድላ ዳኛቸው እንደሚያስረዱት ክለቦች በየትኛውም ዘመናዊ የህክምና ተቋም የኤምአርአይ ምርመራቸውን ካከናወኑ በኋላ የፌደሬሽኑ  የቴክኒክ እና የህክምና ኮሚቴዎችን ተጨማሪ ማረጋገጫ ማድረግ ነበረባቸው፡፡ እንደ አቶ ተድላ ዳኛቸው ገለፃ ከኤምአርአይ ምርመራው ሌላ ኮሚቴዎቹ  በተለያዩ መንገዶች የተጨዋቾችን እድሜ ለማጣራት የሰሩት አንዳንድ የማጭበርበር ሁኔታዎችን ለማስቀረትነው፡፡ በዚህም መሰረት የህክምና ኮሚቴው የእያንዳንዱን ክለብ ተጨዋቾች  ወደ ስታድዬም ጠርቶ በአጠቃላይ ተክለሰውነታቸውን ገምግሟል፡፡ ማንኛውም ተጨዋች በሁሉም  ምርመራዎች የእድሜው ትክክለኛነት ካላረጋገጠ መጫወት አይችልም፡፡ ከ17 ዓመት በታች በተዘጋጀው የታዳጊዎች ውድድር ላይ የሚሳተፉ ክለቦች በስብስባቸው የሚይዟቸው ተጨዋቾች እድሜያቸው 15 እና 16 ዓመት  መሆን ሲገባው ይህን የእድሜ ገደብ በሟሟላት እስከ 25 ተጨዋቾች ያስመዘግባሉ፡፡  ክለቦች ውድድሩ ከመጀመሩ በፊት የያዟቸውን ተጨዋቾች እድሜ በሁሉም ምርመራዎች እንዲያረጋግጡ በቂ ጊዜ ተሰጥቷቸው ነበር፡፡ እስከ የካቲት 15  የተሰጠው ቀነ ገደብ ዛሬ ያልቃል፡፡ ከዛሬ በፊት ብዙዎቹ ክለቦች የምርመራ ሂደቱን እንዳጠናቀቁ የሚናገሩት አቶ ተድላ፤ አንዳንድ ክለቦች ቢዘገዩም  በአስቸኳይ አስፈላጊውን መመርያ ተከትለው እንዲሰሩ በማበረታት ውድድሩ ከመጀመሩ በፊት የማጣራት ሂደቱን እንዲጨርሱ ጥረት እያደረግን ነው ብለዋል፡፡ በማዕከላዊ ዞን ካሉት ክለቦች ቅዱስ ጊዮርጊስ፤ ደደቢት፤ መከላከያ፤ ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ሁሉንም መስፈርቶች በሟሟላት እና በማረጋገጥ  የውድድሩን መጀመር በመጠባበቅ ላይ ናቸው፡፡ አርባምንጭ ከነማ እና ሃዋሳ ከነማ ግን ትንሽ ቢዘገዩም በቀጣይ ሳምንት የምርመራውን ሂደት እንደሚጨርሱ ተስፋ ተደርጓል፡፡
የእግር ኳስ ፌደሬሽኑ ከምንጊዜውም በላይ በኢትዮጵያ እግር ኳስ ያለውን የእድሜ ማጭበርበር ችግር ለመፍታት ቁርጠኛ አቋም መያዙን የገለፁት የውድድር ዋና የስራ ሂደት ሃላፊ አቶ ተድላ ዳኛቸው፤ የተጨዋቾች መረጃ  በትክክለኛ መንገድ  ተሰርቶ በዘመናዊ የመረጃ ክምችት  መቀመጥ  ስላለበት የምርመራ ሂደቶችን በትኩረት መከናወናቸውን ያስረዳሉ፡፡ ከታዳጊዎች ውድድሩ ጋር በተያያዘ የተጨዋቾች ምዝገባ የተከናወነው አለም አቀፍ መመርያን በመከተል ነው፡፡ በዚህ መሰረትም በእግር ኳስ ፌደሬሽኑ አሰራር በትክክለኛ ምርመራዎች እድሜው ተረጋግጦ የተመዘገበ ተጨዋች ወደፊት እድሜውን ሊጨምር ወይንም ሊቀንስ የማይቻልበት ሁኔታ ተፈጥሯል፡፡
የውድድሩ አካሄድ እና ጠቀሜታዎች
ከ17 ዓመት በታች የሚካሄደው የታዳጊዎች ውድድር በአንድ ዙር እንደሚደረግ የተናገሩት የውድድር ዋና የስራ ሂደት ሃላፊው፤ የየክለቦቹ ተጨዋቾች ተማሪዎች እንደመሆናቸው ከውድድሩ በተያያዘ ትምህርታቸውን እንዳያስተጓጉልባቸው በሳምንት አንዴ ጨዋታዎችን ለማካሄድ እንደተወሰነና ታዳጊዎቹ በየስታድዬሞቹ በቂ ተመልካች እንዲያገኙ  ከተለያዩ የፕሪሚዬር ሊግና ሌሎች ውድድሮች ጋር ጎን ለጎን በማካሄድ  የፉክክር መንፈሱን ለማሟሟቅ መታሰቡን ገልፀዋል፡፡ በታዳጊዎች ውድድሩ ለሚያሸንፍ ክለብ ልዩ ዋንጫ መዘጋጀቱ እንደማይቀር የጠቀሱት የውድድር ዋና የስራ ሂደት ሃላፊ አቶ ተድላ ዳኛቸው፤ በታዳጊ ደረጃ የሚደረግ ውድድርን በተለያየ የማበረታቻ ድጋፎች ማስኬድ መሰረታዊ ጥቅም ስለሚኖረው የእግር ኳስ ፌደሬሽኑ ስራ አስፈፃሚ በዚህ ረገድ ትኩረት እንደሚሰጥ አስባለሁ ብለዋል፡፡
የፕሪሚዬር ሊግ ክለቦች በታዳጊዎች ውድድር በመሳተፋቸው በርካታ ጥቅሞችን እንደሚያገኙ የውድድር ዋና የስራ ሂደት ሃላፊው ያስገነዝባሉ፡፡ የመጀመርያው  ጥቅም ውድድሩ ለዋና ቡድናቸው በቂ እና ብቁ ተተኪ ተጨዋቾችን የሚያሳድጉበት እድል ለክለቦች ይፈጠርላቸዋል፡፡ ዋና ቡድናቸውን ለማጠናከር ብቻ ሳይሆን ክለቦች በተጨዋቾች የዝውውር ገበያ ከፍተኛ ወጪ የሚያወጡበትንም ሁኔታ የሚያስቀርና ከራሳቸው አልፎ ለሌሎች ክለቦች ወጣት ተጨዋቾችን በዝውውር ገበያ በማቅረብ ገቢ ሊያገኙበት ይችላሉ፡፡ ከክለቦች ተጠቃሚነት ባሻገር ከፍተኛው ውጤት ክለቦች ለብሄራዊ ቡድን ወጣት እና ተተኪ ተጨዋቾችን በየጊዜው እንዲያፈሩ የሚያስችል መሆኑ ነው፡፡  በ2015 እኤአ ኒጀር ላይ በሚደረገው የአፍሪካ የሀ-17 ሻምፒዮና ኢትዮጵያ እንደምትሳተፍ አያይዘው ያነሱት አቶ ተድላ ዳኛቸው፤  በዚህ አህጉራዊ ሻምፒዮና ለሚሳተፈው የኢትዮጵያ ሀ 17 ብሄራዊ ቡድን የሚበቁ ተጨዋቾችን ለማግኘት ውድድሩ አመቺ መድረክ ይሆናል ብለዋል፡፡
በውድድሩ  ክለቦች በዋናነት በስልጠና ወጥ አሰራር እንዲኖራቸው ይደረጋል ያሉት  አቶ ተድላ ዳኛቸው፤  በየክለቡ ታዳጊዎችን የሚያሰለጥኑ አሰልጣኞች ብቃታቸው እንደሚመዘን ወጥ የሆነ የስልጠና መመርያ ተከትለው እንዲሰሩ እና እንዲወዳደሩ ጥረት እንደሚደረግ አስገንዝበው፤ ለዚህም  የኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌደሬሽን የቴክኒክ ዲፓርትመንት የስልጠና ማንዋል በመስራትና አሰልጣኞች ብቃታቸውን የሚያሳድጉባቸው ሴሚናሮች በማዘጋጀት እንደሚንቀሳቀስ በመግለፅም ታዳጊዎች  በወጥ  የስልጠና ሂደት በማለፍ ለብሄራዊ ቡድን ደረጃ ሲደርሱ በተመሳሳይ ብቃት እና አቋም እንዲኖራቸው ያስችላል ብለዋል፡፡
በክለቦች ህጋዊነት ሰርተፍኬት ያለው ወቅታዊ ሁኔታ
ከ17 ዓመት በታች በሚደረገው የታዳጊዎች ውድድር ላይ ክለቦች ቡድኖችን በማቋቋም መሳተፋቸው በአፍሪካ እግር ኳስ ኮንፌደሬሽንን የሚጠየቀውን የአንድ እግር ኳስ ክለብ መመዘኛ ለሟሟላት ወሳኝ መሆኑን የሚገልፁት የውድድር ዋና የስራ ሂደት ሃላፊ አቶ ተድላ ዳኛቸው፤  የክለቦች ህጋዊነት ሰርተፍኬትን በየደረጃው በማግኘት በአህጉራዊ ውድድሮች ለመሳተፍ የሚያስችላቸውን ሁኔታ የሚፈጥር መሆኑን  ያስረዳሉ፡፡ በአፍሪካ እግር ኳስ ኮንፌደሬሽን በወጣ መመርያ መሰረት አንድ ክለብ በውድድር ሲሳተፍ ሊያሟላቸው የሚገቡ መስፈርቶች አሉ፡፡ እነዚህን መስፈርቶች የአፍሪካ እግር ኳስ ፌደሬሽን ያወጣው ያለምክንያት አይደለም፡፡ በሚያዘጋጃቸው አህጉራዊ ውድድሮች ለክለቦች የመሳተፍ ፍቃድ የሚሰጠው ተገቢውን መስፈርት አሟልተው የክለቦች ህጋዊነት ሰርተፍኬት ያገኙትን ብቻ  ነው፡፡  ክለቦች ይሄው የአፍሪካ እግር ኳስ ኮንፌደሬሽን መመርያ ተገልጾላቸው የተቀመጡትን መመዘኛ መስፈርቶች እንዲያሟሉ ከተነገራቸው ሶስተ ዓመታት አልፈዋል፡፡ ከመስፈርቶቹ መካከል በቅድሚያ ክለቦች በአደረጃጀታቸው በወጣቶች ላይ የተመሰረት መዋቅር  እንዲኖራቸው ያስፈልጋል፤ ይህም የእግር ኳሱን ወጥ እድገት ለመቀጠል ወሳኝ ስለሆነ ነው፡፡
ክለቦች በታዳጊዎች እና በወጣቶች ስልጠና ሊያሰሯቸው የሚችሏቸው ብቁ አሰልጣኞች እንዲኖሯቸው ይጠየቃል፡፡ አንድ በፕሪሚዬር ሊግ ደረጃ ተወዳዳሪ የሆነ ክለብ ክለብ የተሟላ ዕህፈት ቤት፤ በቂ የፋይናንሻል አቅም ፤ የስፖርት ማዘውተርያ ስፍራ፤ የተሟላ የባለሙያዎች አደረጃጀት ሊኖረው ይገባል፡፡ በእነዚህ መስፈርቶች መሰረት ክለቦች  በሶስት  ደረጃዎች በኤ፤ ቢ እና ሲ በመመዘን የህጋዊነት ሰርተፍኬት ይሰጣቸዋል፡፡ የህጋዊነት ሰርተፍኬቱን ለመስጠት የእግር ኳስ ፌደሬሽኑ የክለቦች አደረጃጀት፤ አቅም አቅም በግንባር እንዲገመግም ሃላፊነት እንደተሰጠው አቶ ተድላ ዳኛቸው ሲናገሩ፤ ለዚህም ተብሎ ሁለት ኮሚቴዎች ተቋቁመው ከአዲሱ ስራ አስፈፃሚ ኮሚቴ ጋር በመተዋወቅ በቅርቡ ስራቸውን ይጀምራሉ ብለዋል፡፡ በክለቦች ህጋዊነት ሰርተፍኬት አሰጣጥ ላይ የሚሰሩት ኮሚቴዎች አንደኛው ቅደመ ውሳኔ የሚሰጥ ሲሆን ሌላኛው የይግባኝ ሰሚ  ነው፡፡ ቅድመ ውሳኔ የሚሰጠው ኮሚቴ በመጀመርያ ውሳኔ ሰጭነቱ ክለቡ ምን አሟልታል በሚል በቂ ግምገማ እና ክትትል በማድረግ የየክለቡን የፍቃድ ደረጃ የሚወስን ይሆናል፡፡ የይግባኝ ሰሚ ኮሚቴው ደግሞ ክለቦች በቅድመ ውሳኔ ሰጪ ኮሚቴው በተሰጣቸው  ደረጃ ላይ ቅሬታ ካላቸው ይግባኝ ብለው የተሰጣቸውን ምዘና ሊያስተካክሉ የሚችሉበት ነው፡፡
አንዳንድ ሁኔታዎችን በመገንዘብ ለመረዳት እንደሚቻለው በክለቦች ህጋዊነት ሰርተፍኬት መመዘኛ ብዙዎቹ  የኢትዮጵያ ክለቦች በሲ ደረጃ ሲሆኑ በቢ ደረጃ ያሉ ጥቂት ናቸው፡፡ በአሁኑ ወቅት በአገሪቱ እግር ኳስ በኤ ደረጃ ሰርተፍኬት የሚያገኝ ክለብ የለም፡፡ በክለቦች ህጋዊነት ሰርተፍኬት እንዲሰጥ መመርያ ያስፈለገው አንድ ክለብ በአህጉራዊ ደረጃ በሚደረጉ ውድድሮች ለመሳተፍ ማሟሟላት  የሚገባው ደረጃዎች ስላሉ ነው፡፡ ክለቦች በዚህ መመርያ መሰረት ሊያሟሉ የሚገባቸውን መስፈርቶች እንዲያሟሉ በፊፋ በኩል የአቅም ግንባታ ስልጠናዎች በተደጋጋሚ ቢሰጡም ብዙም እየተራመዱ አይደለም፡፡  የፐሪሚዬር ሊግ  ክለቦች አስቀድመው የሴቶች ቡድን በማቋቋም ተንቀሳቀሰው አሁን ውድድር እየተደረገ ውጤቱን በማየት ላይ ናቸው፡፡ ከቅርብ ጊዜ ወዲህ ደግሞ የሀ 17 ቡድኖች መያዛቸው አንዱ ርምጃ ሲሆን አንዳንድ ክለቦች የቴክኒክ ዲያሬክተር መቅጠራቸው፤ በማርኬቲንግ ባለሙያ መስራትም መጀመራቸውም እንደለውጥ የሚታይ ቢሆንም ገና ብዙ መስራት ይጠበቅባቸዋል፡፡

           በ2014 የአፍሪካ ክለቦች ሻምፒዮንስ ሊግ የአምናው የፕሪሚዬር ሊግ ሻምፒዮን ደደቢት ወደ አንደኛ ዙር ማጣርያ ማለፉን አረጋገጠ፡፡ በሌላ በኩል በ2014 የአፍሪካ ክለቦች ኮንፌደሬሽን ካፕ  ቅድመ ማጣሪያ በሁለቱም ጨዋታ የተሸነፈው መከላከያ ከውድድሩ ውጭ ሆኗል። ባለፈው ሰሞን በአፍሪካ ክለቦች ሻምፒዮንስ ሊግ የቅድመ ማጣርያ የመልስ ጨዋታ  ደደቢት ከሜዳው ውጭ በዛንዚባሩ ኬኤምኬኤም 2ለ0 ቢሸነፍም፤ በአጠቃላይ የደርሶ መልስ ውጤት 3ለ2 አሸንፏል።  በኮንፌደሬሽን ካፕ ቅድመ መጣርያ የመልስ ጨዋታ ሊዮፓርድስን በሜዳው ያስተናገደው የአምናው የጥሎ ማለፍ ሻምፒዮን መከላከያ 2ለ0 ተሸንፎ በአጠቃላይ ውጤት 4ለ0 ተረትቶ ከውድድሩ ተሰናብቷል፡፡ በአፍሪካ ክለቦች ሻምፒዮንስ ሊግ አንደኛ ዙር የማጣርያ ምእራፍ ኢትዮጵያን የወከለው ደደቢት የሚገናኘው  ከቱኒዚያው ክለብ ሲኤስ ሴፋክሲዬን ጋር ነው፡፡ ደደቢት ከቱኒዚያው ክለብ ጋር የደርሶ መልስ ትንቅንቁን ከሳምንት በኋላ በሜዳው ይጀምራል፡፡  
መከላከያ ትኩረቱን ወደ ሊጉ ይመልሳል
በ2014 የአፍሪካ ክለቦች ኮንፌደሬሽን ካፕ የቅድመ ማጣርያ የመልስ ጨዋታዎች ወደ አንደኛ ዙር ለመግባት 11 ክለቦች እድል ነበራቸው፡፡ ባለፈው የውድድር ዘመን የጥሎ ማለፍ አሸናፊ የነበረው መከላከያ ከታላቁ የኬንያ ክለብ ጋር በመደልደሉ ቅድመ ማጣርያውን ማለፍ አልቻለም፡፡ መከላከያ ትኩረቱን ወደ ፕሪሚዬር ሊጉ በመመለስ ለዋንጫ ተፎካካሪ እንደሚሆን ተገምቷል። መከላከያ ከዘንድሮ በፊት በአፍሪካ ደረጃ በሁለት የውድድር ዘመናት የተሳትፎ ልምድ ነበረው፡፡ ለመጀመርያ ጊዜ ድሮ “ካፕዊነርስ ካፕ” ተብሎ በሚጠራው የጥሎ ማለፍ ዋንጫ በ1976 እኤአ ተሳትፏል፡፡ በወቅቱም እስከ ሩብ ፍፃሜ ለመጓዝ በቅቶ ነበር፡፡ በ2007 እኤአ ላይ ደግሞ በኮንፌደሬሽን ካፕ ሲሳተፍ ቅድመ ማጣርያውን አልፎ ነበር፡፡ ከዚያ በመጀመርያው ዙር ክለብ በሆነ የደርሶ መልስ ውጤት ተሸንፎ ከውድድሩ ውጭ ሆኗል፡፡
ደደቢት 3 ኬኤምኬኤም 2
በ2014 የአፍሪካ ክለቦች ሻምፒዮንስ ሊግ ከሳምንት በፊት በቅድመ ማጣርያ የመልስ ጨዋታዎች 14 ክለቦች ወደ አንደኛ ዙር ማጣርያ ማለፋቸውን አረጋግጠዋል፡፡ አምና የኢትዮጵያ ፕሪሚዬር ሊግን በታሪክ ለመጀመሪያ ጊዜ ያሸነፈው ደደቢት በኢትዮጵያ የክለቦች ውድድር በአጭር ጊዜ ስኬታማ በመሆን ከመደነቁም በላይ ለዋናው ብሄራዊ ቡድን ባለው አስተዋፅኦም የተለየ ነው፡፡ በ2011 እና በ2012 እኤአ የጥሎ ማለፍ ሻምፒዮን ለመሆን የበቃው ደደቢት ለዚህ ውጤቱ በሁለት የውድድር ዘመን የአፍሪካ ክለቦች ኮንፌዴሬሽን ካፕን ለመሳተፍ ልምድ አለው፡፡ በአፍሪካ ክለቦች ሻምፒዮንስ ሊግ ኢትየጵያን ሲወክል ግን ዘንድሮ ለመጀመሪያ ጊዜ ነው፡፡
በሻምፒዮንስ ሊጉ የመጀመሪያ ዙር ማጣርያ የደደቢት ተጋጣሚ የሆነው የቱኒዚያው ክለብ ሴፋክስዬን በስኬት እና በምርጥነት ከአፍሪካ 5 ታላላቅ ክለቦች ተርታ የሚሰለፍ ነው፡፡ የቱኒዚያ ፕሪሚዬር ሊግን ለ8 ጊዜ ያሸነፈው ሴፋክስዬን በአፍሪካ ሻምፒዮንስ ሊግ ሁለት ጊዜ በነበረው ተሳትፎ በ2006 ኤአ ላይ ሁለተኛ ደረጃ ያገኘበት ውጤት ከፍተኛው ነበር፡፡ በኮንፌደሬሽን ካፕ ደግሞ በ2007፤ በ2008 እና በ2013 እኤአ ለሶስት ጊዜያት ዋንጫውን በማንሳት እና በ2008 እና 20009 እኤአ በካፍ ሱፕር ካፕ ሁለተኛ ደረጃን አከታትሎ አስመዝግቧል፡፡
በቱኒዚያዊው አሰልጣኝ ሃመዲ ዳው የሚመራው ሴፋክሴዬን በተጨዋቾች ስብስቡ የካሜሮን፤ የጋና፤ የአይቬሪኮስት፤ የጋቦንና የሞሮኮ ተጨዋቾችን ያካተተ ሲሆን አጠቃላይ 26 ተጨዋቾች የሚገኙበት ስብስቡ በትራንስፈርማርኬት የዝውውር ገበያ ስሌት 8 ሚሊዮን 750ሺ ዩሮ የተተመነ ነው፡፡ 3152 የተመዘገቡ አባላት ያሉት ሴፋክሴዬን በሜዳነት የሚጠቀመወ 12ሺ ተመልካች የሚያስተናግደውን ስታዴ ታሌብ ማሃሪ ስታድዬምን    ነው፡፡

Saturday, 22 February 2014 13:21

ወንጀል

“ቨርጂኒያ “ጂንጀር” ላይትሌይ በቴክሳስ ምስራቃዊ ክፍል ኮሬይቪል ኮፊ ኬክስ በሚባል ስም የሚታወቀው በጣም ዝነኛ የኬክ መጋገሪያ ድርጅት ባለቤት ነች፡፡ የራሷ ፈጠራ ብቻ የሆነውን የኬክ ጣዕም ለመቅመስ ደንበኞቿ ከሩቅ ቦታ ወደ ትንሿ መደብር ይመጣሉ። አንድ ወጣት ልጅ ዝነኛ ኬኳን ከበላ በኋላ ከተማው ውስጥ ሞቶ ስለተገኘ ለመላው ማህበረሰብ እጅግ አስደንጋጭ ነገር ሆነ። በቅርቡ በኃላፊነት የተሾመው የፖሊስ አዛዥ ለጉዳዩ አስቸኳይ ዕልባት ለመስጠት ቃል ተብቷል፡፡ ጂንጀር ልትረዳው ብትፈልግም፣ እሱ ግን ድርጅቷ ውስጥ ተቀጣሪ የሆነን ሰው በግድያ ወንጀል ከሰሰ፡፡ እሷ ደግሞ ወጣቱ የፖሊስ አዛዥ ስለግድያ ወንጀሉ የደረሰበትን ድምዳሜ ስላለመነችበት ተቃወመችና ወንጀለኛውን ለማወቅ በምስጢር ራሷ ወንጀሉን መከታተል ጀመረች።”
ርዕስ- ጣፋጭ ጂንጀር መርዝ (Sweet Ginjer Poison)
ደራሲ - ሮበርት በርተን ሮቢንሰን
ተርጓሚ - አምሳሉ ጌታሁን ደርሰህ
ዋጋ 35 ብር
ህትመት - ላንጋኖ ማተሚያ ቤት