Administrator

Administrator

        የኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌደሬሽን ለፕሪሚዬር ሊግ ክለቦች ከ17 ዓመት በታች የታዳጊ ውድድር ከሳምንት በኋላ ይጀምራል፡፡ የታዳጊዎችን ውድድርን በጥራት ለመምራት ከፍተኛ ትኩረት የሰጠው የእግር ኳስ ፌዴሬሽኑ በውድድሩ ተሳታፊ በሚሆኑ ክለቦች ላይ አስፈላጊውን  የእድሜ ማጣራት በማከናወን ከሞላ ጎደል ዝግጅቱን እንዳጠናቀቀ  ለማወቅ ተችሏል፡፡ በውድድሩ ከ17 ዓመት በታች ቡድናቸውን የሚያሳትፉ የፕሪሚዬር ሊግ ክለቦች ለተጨዋቾቻቸው የተዘጋጀውን የእድሜ ማረጋገጫ ምርመራ በኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌደሬሽን የህክምና ኮሚቴ የግምባር ፍተሻ እና በቴክኒክ ኮሚቴው ተጨማሪ ማረጋገጫ መሰረት አከናውነዋል፡፡  ከ17 ዓመት በታች የታዳጊዎች ውድድሩ የካቲት 22 እንደሚጀመር የገለፀው የኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌደሬሽን ተሳታፊ ክለቦች አስፈላጊውን ዝግጅት እንዲያደርጉ ጥሪ ያስተላለፈ ሲሆን ዘንድሮ ተሳታፊ የሆኑ ክለቦች ብዛት 9 እንደሆኑና ውድድድራቸውን በደቡብ እና በማዕከላዊ ዞኖች በመከፋፈል እንደሚያደርጉ አስታውቋል፡፡ በማዕከላዊ ዞን  ቅዱስ ጊዮርጊስ፤ ኢትዮጵያ ቡና፤ ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ፤ ደደቢት፤ መብራት ሃይልና ሙገር ሲምንቶ ሲመደቡ፤ በደቡብ ዞን ደግሞ አርባምንጭ ፤ ሲዳማ ቡና እና ሃዋሳ ከነማ ይገኛሉ፡፡
ከ17 ዓመት በታች ውድድሩ የተዘጋጀው በታዳጊዎች ላይ በመስራት የአገሪቱን እግር ኳስ እድገት በጠንካራ መሰረት ላይ ለመጣል ያስችላል ተብሎ ነው የእግር ኳስ ፌደሬሽኑ ለውድድሩ ከፍተኛ ትኩረት በመስጠት ተተኪ ተጨዋቾችን ለብሄራዊ ቡድን ለማፍራት እንደሚንቀሳቀስ  ስፖርት አድማስ ያነጋገራቸው የእግር ኳስ ፌዴሬሽኑ የውድድር ዋና ስራ ሂደት ሃላፊ አቶ ተድላ ዳኛቸው ተናግረዋል፡፡ በኢትዮጵያ እግር ኳስ  የታዳጊዎችን ውድድር ለማካሄድ በፌደሬሽን በኩል እንቅስቃሴው ከተጀመረ ቢቆይም ተግባራዊነቱ አልተሳካም ነበር፡፡ በቀድሞ የፌደሬሽን ስራ አስፈፃሚ የሴቶች እግር ኳስ  ቡድኖችን ከማቋቋም ባሻገር የፕሪሚዬር ሊግ ክለቦች የታዳጊ ቡድኖች እንዲኖራቸውና ውድድር እንዲያካሂዱ ከስምምነት ላይ ተደርሶ እንደነበር ያስታወሱት አቶ ተድላ ዳኛቸው፤ አሁን ያለው አዲስ የስራ አስፈፃሚ ኮሚቴም በወጣቶች ላይ መስራት ለእግር ኳሱ እድገት ወሳኝ አቅጣጫ ነው በማለት የታዳጊዎች ውድድሩን ተግባራዊ ለማድረግ መወሰኑን ይገልፃሉ፡፡
የእድሜ ማረጋገጫ ምርመራዎች
አንድ ክለብ የሀ 17 ቡድን ሲመሰርት ማሟላት ያለበት መስፈርቶች በእግር ኳስ ፌደሬሽኑ በኩል ተቀምጠዋል፡፡ የመጀመርያው የተጨዋቾች የእድሜ ገደብን ማሟላትና ማረጋገጥ ነው፡፡ ይህ ደግሞ ክለቦች በዘመናዊ የህክምና ምርመራ በማከናወን በሚያቀርቡት ማስረጃ ብቻ ሳይሆን በፌዴሬሽኑ የህክምና ኮሚቴ በኩል በግምባር የተጨዋቾችን ተክለሰውነት በተለያዩ ዘዴዎች በመፈተሽ በሚካሄድ  ምርመራ  መረጋገጥ ይኖርበታል፡፡ አቶ ተድላ ዳኛቸው እንደሚያስረዱት ክለቦች በየትኛውም ዘመናዊ የህክምና ተቋም የኤምአርአይ ምርመራቸውን ካከናወኑ በኋላ የፌደሬሽኑ  የቴክኒክ እና የህክምና ኮሚቴዎችን ተጨማሪ ማረጋገጫ ማድረግ ነበረባቸው፡፡ እንደ አቶ ተድላ ዳኛቸው ገለፃ ከኤምአርአይ ምርመራው ሌላ ኮሚቴዎቹ  በተለያዩ መንገዶች የተጨዋቾችን እድሜ ለማጣራት የሰሩት አንዳንድ የማጭበርበር ሁኔታዎችን ለማስቀረትነው፡፡ በዚህም መሰረት የህክምና ኮሚቴው የእያንዳንዱን ክለብ ተጨዋቾች  ወደ ስታድዬም ጠርቶ በአጠቃላይ ተክለሰውነታቸውን ገምግሟል፡፡ ማንኛውም ተጨዋች በሁሉም  ምርመራዎች የእድሜው ትክክለኛነት ካላረጋገጠ መጫወት አይችልም፡፡ ከ17 ዓመት በታች በተዘጋጀው የታዳጊዎች ውድድር ላይ የሚሳተፉ ክለቦች በስብስባቸው የሚይዟቸው ተጨዋቾች እድሜያቸው 15 እና 16 ዓመት  መሆን ሲገባው ይህን የእድሜ ገደብ በሟሟላት እስከ 25 ተጨዋቾች ያስመዘግባሉ፡፡  ክለቦች ውድድሩ ከመጀመሩ በፊት የያዟቸውን ተጨዋቾች እድሜ በሁሉም ምርመራዎች እንዲያረጋግጡ በቂ ጊዜ ተሰጥቷቸው ነበር፡፡ እስከ የካቲት 15  የተሰጠው ቀነ ገደብ ዛሬ ያልቃል፡፡ ከዛሬ በፊት ብዙዎቹ ክለቦች የምርመራ ሂደቱን እንዳጠናቀቁ የሚናገሩት አቶ ተድላ፤ አንዳንድ ክለቦች ቢዘገዩም  በአስቸኳይ አስፈላጊውን መመርያ ተከትለው እንዲሰሩ በማበረታት ውድድሩ ከመጀመሩ በፊት የማጣራት ሂደቱን እንዲጨርሱ ጥረት እያደረግን ነው ብለዋል፡፡ በማዕከላዊ ዞን ካሉት ክለቦች ቅዱስ ጊዮርጊስ፤ ደደቢት፤ መከላከያ፤ ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ሁሉንም መስፈርቶች በሟሟላት እና በማረጋገጥ  የውድድሩን መጀመር በመጠባበቅ ላይ ናቸው፡፡ አርባምንጭ ከነማ እና ሃዋሳ ከነማ ግን ትንሽ ቢዘገዩም በቀጣይ ሳምንት የምርመራውን ሂደት እንደሚጨርሱ ተስፋ ተደርጓል፡፡
የእግር ኳስ ፌደሬሽኑ ከምንጊዜውም በላይ በኢትዮጵያ እግር ኳስ ያለውን የእድሜ ማጭበርበር ችግር ለመፍታት ቁርጠኛ አቋም መያዙን የገለፁት የውድድር ዋና የስራ ሂደት ሃላፊ አቶ ተድላ ዳኛቸው፤ የተጨዋቾች መረጃ  በትክክለኛ መንገድ  ተሰርቶ በዘመናዊ የመረጃ ክምችት  መቀመጥ  ስላለበት የምርመራ ሂደቶችን በትኩረት መከናወናቸውን ያስረዳሉ፡፡ ከታዳጊዎች ውድድሩ ጋር በተያያዘ የተጨዋቾች ምዝገባ የተከናወነው አለም አቀፍ መመርያን በመከተል ነው፡፡ በዚህ መሰረትም በእግር ኳስ ፌደሬሽኑ አሰራር በትክክለኛ ምርመራዎች እድሜው ተረጋግጦ የተመዘገበ ተጨዋች ወደፊት እድሜውን ሊጨምር ወይንም ሊቀንስ የማይቻልበት ሁኔታ ተፈጥሯል፡፡
የውድድሩ አካሄድ እና ጠቀሜታዎች
ከ17 ዓመት በታች የሚካሄደው የታዳጊዎች ውድድር በአንድ ዙር እንደሚደረግ የተናገሩት የውድድር ዋና የስራ ሂደት ሃላፊው፤ የየክለቦቹ ተጨዋቾች ተማሪዎች እንደመሆናቸው ከውድድሩ በተያያዘ ትምህርታቸውን እንዳያስተጓጉልባቸው በሳምንት አንዴ ጨዋታዎችን ለማካሄድ እንደተወሰነና ታዳጊዎቹ በየስታድዬሞቹ በቂ ተመልካች እንዲያገኙ  ከተለያዩ የፕሪሚዬር ሊግና ሌሎች ውድድሮች ጋር ጎን ለጎን በማካሄድ  የፉክክር መንፈሱን ለማሟሟቅ መታሰቡን ገልፀዋል፡፡ በታዳጊዎች ውድድሩ ለሚያሸንፍ ክለብ ልዩ ዋንጫ መዘጋጀቱ እንደማይቀር የጠቀሱት የውድድር ዋና የስራ ሂደት ሃላፊ አቶ ተድላ ዳኛቸው፤ በታዳጊ ደረጃ የሚደረግ ውድድርን በተለያየ የማበረታቻ ድጋፎች ማስኬድ መሰረታዊ ጥቅም ስለሚኖረው የእግር ኳስ ፌደሬሽኑ ስራ አስፈፃሚ በዚህ ረገድ ትኩረት እንደሚሰጥ አስባለሁ ብለዋል፡፡
የፕሪሚዬር ሊግ ክለቦች በታዳጊዎች ውድድር በመሳተፋቸው በርካታ ጥቅሞችን እንደሚያገኙ የውድድር ዋና የስራ ሂደት ሃላፊው ያስገነዝባሉ፡፡ የመጀመርያው  ጥቅም ውድድሩ ለዋና ቡድናቸው በቂ እና ብቁ ተተኪ ተጨዋቾችን የሚያሳድጉበት እድል ለክለቦች ይፈጠርላቸዋል፡፡ ዋና ቡድናቸውን ለማጠናከር ብቻ ሳይሆን ክለቦች በተጨዋቾች የዝውውር ገበያ ከፍተኛ ወጪ የሚያወጡበትንም ሁኔታ የሚያስቀርና ከራሳቸው አልፎ ለሌሎች ክለቦች ወጣት ተጨዋቾችን በዝውውር ገበያ በማቅረብ ገቢ ሊያገኙበት ይችላሉ፡፡ ከክለቦች ተጠቃሚነት ባሻገር ከፍተኛው ውጤት ክለቦች ለብሄራዊ ቡድን ወጣት እና ተተኪ ተጨዋቾችን በየጊዜው እንዲያፈሩ የሚያስችል መሆኑ ነው፡፡  በ2015 እኤአ ኒጀር ላይ በሚደረገው የአፍሪካ የሀ-17 ሻምፒዮና ኢትዮጵያ እንደምትሳተፍ አያይዘው ያነሱት አቶ ተድላ ዳኛቸው፤  በዚህ አህጉራዊ ሻምፒዮና ለሚሳተፈው የኢትዮጵያ ሀ 17 ብሄራዊ ቡድን የሚበቁ ተጨዋቾችን ለማግኘት ውድድሩ አመቺ መድረክ ይሆናል ብለዋል፡፡
በውድድሩ  ክለቦች በዋናነት በስልጠና ወጥ አሰራር እንዲኖራቸው ይደረጋል ያሉት  አቶ ተድላ ዳኛቸው፤  በየክለቡ ታዳጊዎችን የሚያሰለጥኑ አሰልጣኞች ብቃታቸው እንደሚመዘን ወጥ የሆነ የስልጠና መመርያ ተከትለው እንዲሰሩ እና እንዲወዳደሩ ጥረት እንደሚደረግ አስገንዝበው፤ ለዚህም  የኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌደሬሽን የቴክኒክ ዲፓርትመንት የስልጠና ማንዋል በመስራትና አሰልጣኞች ብቃታቸውን የሚያሳድጉባቸው ሴሚናሮች በማዘጋጀት እንደሚንቀሳቀስ በመግለፅም ታዳጊዎች  በወጥ  የስልጠና ሂደት በማለፍ ለብሄራዊ ቡድን ደረጃ ሲደርሱ በተመሳሳይ ብቃት እና አቋም እንዲኖራቸው ያስችላል ብለዋል፡፡
በክለቦች ህጋዊነት ሰርተፍኬት ያለው ወቅታዊ ሁኔታ
ከ17 ዓመት በታች በሚደረገው የታዳጊዎች ውድድር ላይ ክለቦች ቡድኖችን በማቋቋም መሳተፋቸው በአፍሪካ እግር ኳስ ኮንፌደሬሽንን የሚጠየቀውን የአንድ እግር ኳስ ክለብ መመዘኛ ለሟሟላት ወሳኝ መሆኑን የሚገልፁት የውድድር ዋና የስራ ሂደት ሃላፊ አቶ ተድላ ዳኛቸው፤  የክለቦች ህጋዊነት ሰርተፍኬትን በየደረጃው በማግኘት በአህጉራዊ ውድድሮች ለመሳተፍ የሚያስችላቸውን ሁኔታ የሚፈጥር መሆኑን  ያስረዳሉ፡፡ በአፍሪካ እግር ኳስ ኮንፌደሬሽን በወጣ መመርያ መሰረት አንድ ክለብ በውድድር ሲሳተፍ ሊያሟላቸው የሚገቡ መስፈርቶች አሉ፡፡ እነዚህን መስፈርቶች የአፍሪካ እግር ኳስ ፌደሬሽን ያወጣው ያለምክንያት አይደለም፡፡ በሚያዘጋጃቸው አህጉራዊ ውድድሮች ለክለቦች የመሳተፍ ፍቃድ የሚሰጠው ተገቢውን መስፈርት አሟልተው የክለቦች ህጋዊነት ሰርተፍኬት ያገኙትን ብቻ  ነው፡፡  ክለቦች ይሄው የአፍሪካ እግር ኳስ ኮንፌደሬሽን መመርያ ተገልጾላቸው የተቀመጡትን መመዘኛ መስፈርቶች እንዲያሟሉ ከተነገራቸው ሶስተ ዓመታት አልፈዋል፡፡ ከመስፈርቶቹ መካከል በቅድሚያ ክለቦች በአደረጃጀታቸው በወጣቶች ላይ የተመሰረት መዋቅር  እንዲኖራቸው ያስፈልጋል፤ ይህም የእግር ኳሱን ወጥ እድገት ለመቀጠል ወሳኝ ስለሆነ ነው፡፡
ክለቦች በታዳጊዎች እና በወጣቶች ስልጠና ሊያሰሯቸው የሚችሏቸው ብቁ አሰልጣኞች እንዲኖሯቸው ይጠየቃል፡፡ አንድ በፕሪሚዬር ሊግ ደረጃ ተወዳዳሪ የሆነ ክለብ ክለብ የተሟላ ዕህፈት ቤት፤ በቂ የፋይናንሻል አቅም ፤ የስፖርት ማዘውተርያ ስፍራ፤ የተሟላ የባለሙያዎች አደረጃጀት ሊኖረው ይገባል፡፡ በእነዚህ መስፈርቶች መሰረት ክለቦች  በሶስት  ደረጃዎች በኤ፤ ቢ እና ሲ በመመዘን የህጋዊነት ሰርተፍኬት ይሰጣቸዋል፡፡ የህጋዊነት ሰርተፍኬቱን ለመስጠት የእግር ኳስ ፌደሬሽኑ የክለቦች አደረጃጀት፤ አቅም አቅም በግንባር እንዲገመግም ሃላፊነት እንደተሰጠው አቶ ተድላ ዳኛቸው ሲናገሩ፤ ለዚህም ተብሎ ሁለት ኮሚቴዎች ተቋቁመው ከአዲሱ ስራ አስፈፃሚ ኮሚቴ ጋር በመተዋወቅ በቅርቡ ስራቸውን ይጀምራሉ ብለዋል፡፡ በክለቦች ህጋዊነት ሰርተፍኬት አሰጣጥ ላይ የሚሰሩት ኮሚቴዎች አንደኛው ቅደመ ውሳኔ የሚሰጥ ሲሆን ሌላኛው የይግባኝ ሰሚ  ነው፡፡ ቅድመ ውሳኔ የሚሰጠው ኮሚቴ በመጀመርያ ውሳኔ ሰጭነቱ ክለቡ ምን አሟልታል በሚል በቂ ግምገማ እና ክትትል በማድረግ የየክለቡን የፍቃድ ደረጃ የሚወስን ይሆናል፡፡ የይግባኝ ሰሚ ኮሚቴው ደግሞ ክለቦች በቅድመ ውሳኔ ሰጪ ኮሚቴው በተሰጣቸው  ደረጃ ላይ ቅሬታ ካላቸው ይግባኝ ብለው የተሰጣቸውን ምዘና ሊያስተካክሉ የሚችሉበት ነው፡፡
አንዳንድ ሁኔታዎችን በመገንዘብ ለመረዳት እንደሚቻለው በክለቦች ህጋዊነት ሰርተፍኬት መመዘኛ ብዙዎቹ  የኢትዮጵያ ክለቦች በሲ ደረጃ ሲሆኑ በቢ ደረጃ ያሉ ጥቂት ናቸው፡፡ በአሁኑ ወቅት በአገሪቱ እግር ኳስ በኤ ደረጃ ሰርተፍኬት የሚያገኝ ክለብ የለም፡፡ በክለቦች ህጋዊነት ሰርተፍኬት እንዲሰጥ መመርያ ያስፈለገው አንድ ክለብ በአህጉራዊ ደረጃ በሚደረጉ ውድድሮች ለመሳተፍ ማሟሟላት  የሚገባው ደረጃዎች ስላሉ ነው፡፡ ክለቦች በዚህ መመርያ መሰረት ሊያሟሉ የሚገባቸውን መስፈርቶች እንዲያሟሉ በፊፋ በኩል የአቅም ግንባታ ስልጠናዎች በተደጋጋሚ ቢሰጡም ብዙም እየተራመዱ አይደለም፡፡  የፐሪሚዬር ሊግ  ክለቦች አስቀድመው የሴቶች ቡድን በማቋቋም ተንቀሳቀሰው አሁን ውድድር እየተደረገ ውጤቱን በማየት ላይ ናቸው፡፡ ከቅርብ ጊዜ ወዲህ ደግሞ የሀ 17 ቡድኖች መያዛቸው አንዱ ርምጃ ሲሆን አንዳንድ ክለቦች የቴክኒክ ዲያሬክተር መቅጠራቸው፤ በማርኬቲንግ ባለሙያ መስራትም መጀመራቸውም እንደለውጥ የሚታይ ቢሆንም ገና ብዙ መስራት ይጠበቅባቸዋል፡፡

           በ2014 የአፍሪካ ክለቦች ሻምፒዮንስ ሊግ የአምናው የፕሪሚዬር ሊግ ሻምፒዮን ደደቢት ወደ አንደኛ ዙር ማጣርያ ማለፉን አረጋገጠ፡፡ በሌላ በኩል በ2014 የአፍሪካ ክለቦች ኮንፌደሬሽን ካፕ  ቅድመ ማጣሪያ በሁለቱም ጨዋታ የተሸነፈው መከላከያ ከውድድሩ ውጭ ሆኗል። ባለፈው ሰሞን በአፍሪካ ክለቦች ሻምፒዮንስ ሊግ የቅድመ ማጣርያ የመልስ ጨዋታ  ደደቢት ከሜዳው ውጭ በዛንዚባሩ ኬኤምኬኤም 2ለ0 ቢሸነፍም፤ በአጠቃላይ የደርሶ መልስ ውጤት 3ለ2 አሸንፏል።  በኮንፌደሬሽን ካፕ ቅድመ መጣርያ የመልስ ጨዋታ ሊዮፓርድስን በሜዳው ያስተናገደው የአምናው የጥሎ ማለፍ ሻምፒዮን መከላከያ 2ለ0 ተሸንፎ በአጠቃላይ ውጤት 4ለ0 ተረትቶ ከውድድሩ ተሰናብቷል፡፡ በአፍሪካ ክለቦች ሻምፒዮንስ ሊግ አንደኛ ዙር የማጣርያ ምእራፍ ኢትዮጵያን የወከለው ደደቢት የሚገናኘው  ከቱኒዚያው ክለብ ሲኤስ ሴፋክሲዬን ጋር ነው፡፡ ደደቢት ከቱኒዚያው ክለብ ጋር የደርሶ መልስ ትንቅንቁን ከሳምንት በኋላ በሜዳው ይጀምራል፡፡  
መከላከያ ትኩረቱን ወደ ሊጉ ይመልሳል
በ2014 የአፍሪካ ክለቦች ኮንፌደሬሽን ካፕ የቅድመ ማጣርያ የመልስ ጨዋታዎች ወደ አንደኛ ዙር ለመግባት 11 ክለቦች እድል ነበራቸው፡፡ ባለፈው የውድድር ዘመን የጥሎ ማለፍ አሸናፊ የነበረው መከላከያ ከታላቁ የኬንያ ክለብ ጋር በመደልደሉ ቅድመ ማጣርያውን ማለፍ አልቻለም፡፡ መከላከያ ትኩረቱን ወደ ፕሪሚዬር ሊጉ በመመለስ ለዋንጫ ተፎካካሪ እንደሚሆን ተገምቷል። መከላከያ ከዘንድሮ በፊት በአፍሪካ ደረጃ በሁለት የውድድር ዘመናት የተሳትፎ ልምድ ነበረው፡፡ ለመጀመርያ ጊዜ ድሮ “ካፕዊነርስ ካፕ” ተብሎ በሚጠራው የጥሎ ማለፍ ዋንጫ በ1976 እኤአ ተሳትፏል፡፡ በወቅቱም እስከ ሩብ ፍፃሜ ለመጓዝ በቅቶ ነበር፡፡ በ2007 እኤአ ላይ ደግሞ በኮንፌደሬሽን ካፕ ሲሳተፍ ቅድመ ማጣርያውን አልፎ ነበር፡፡ ከዚያ በመጀመርያው ዙር ክለብ በሆነ የደርሶ መልስ ውጤት ተሸንፎ ከውድድሩ ውጭ ሆኗል፡፡
ደደቢት 3 ኬኤምኬኤም 2
በ2014 የአፍሪካ ክለቦች ሻምፒዮንስ ሊግ ከሳምንት በፊት በቅድመ ማጣርያ የመልስ ጨዋታዎች 14 ክለቦች ወደ አንደኛ ዙር ማጣርያ ማለፋቸውን አረጋግጠዋል፡፡ አምና የኢትዮጵያ ፕሪሚዬር ሊግን በታሪክ ለመጀመሪያ ጊዜ ያሸነፈው ደደቢት በኢትዮጵያ የክለቦች ውድድር በአጭር ጊዜ ስኬታማ በመሆን ከመደነቁም በላይ ለዋናው ብሄራዊ ቡድን ባለው አስተዋፅኦም የተለየ ነው፡፡ በ2011 እና በ2012 እኤአ የጥሎ ማለፍ ሻምፒዮን ለመሆን የበቃው ደደቢት ለዚህ ውጤቱ በሁለት የውድድር ዘመን የአፍሪካ ክለቦች ኮንፌዴሬሽን ካፕን ለመሳተፍ ልምድ አለው፡፡ በአፍሪካ ክለቦች ሻምፒዮንስ ሊግ ኢትየጵያን ሲወክል ግን ዘንድሮ ለመጀመሪያ ጊዜ ነው፡፡
በሻምፒዮንስ ሊጉ የመጀመሪያ ዙር ማጣርያ የደደቢት ተጋጣሚ የሆነው የቱኒዚያው ክለብ ሴፋክስዬን በስኬት እና በምርጥነት ከአፍሪካ 5 ታላላቅ ክለቦች ተርታ የሚሰለፍ ነው፡፡ የቱኒዚያ ፕሪሚዬር ሊግን ለ8 ጊዜ ያሸነፈው ሴፋክስዬን በአፍሪካ ሻምፒዮንስ ሊግ ሁለት ጊዜ በነበረው ተሳትፎ በ2006 ኤአ ላይ ሁለተኛ ደረጃ ያገኘበት ውጤት ከፍተኛው ነበር፡፡ በኮንፌደሬሽን ካፕ ደግሞ በ2007፤ በ2008 እና በ2013 እኤአ ለሶስት ጊዜያት ዋንጫውን በማንሳት እና በ2008 እና 20009 እኤአ በካፍ ሱፕር ካፕ ሁለተኛ ደረጃን አከታትሎ አስመዝግቧል፡፡
በቱኒዚያዊው አሰልጣኝ ሃመዲ ዳው የሚመራው ሴፋክሴዬን በተጨዋቾች ስብስቡ የካሜሮን፤ የጋና፤ የአይቬሪኮስት፤ የጋቦንና የሞሮኮ ተጨዋቾችን ያካተተ ሲሆን አጠቃላይ 26 ተጨዋቾች የሚገኙበት ስብስቡ በትራንስፈርማርኬት የዝውውር ገበያ ስሌት 8 ሚሊዮን 750ሺ ዩሮ የተተመነ ነው፡፡ 3152 የተመዘገቡ አባላት ያሉት ሴፋክሴዬን በሜዳነት የሚጠቀመወ 12ሺ ተመልካች የሚያስተናግደውን ስታዴ ታሌብ ማሃሪ ስታድዬምን    ነው፡፡

Saturday, 22 February 2014 13:21

ወንጀል

“ቨርጂኒያ “ጂንጀር” ላይትሌይ በቴክሳስ ምስራቃዊ ክፍል ኮሬይቪል ኮፊ ኬክስ በሚባል ስም የሚታወቀው በጣም ዝነኛ የኬክ መጋገሪያ ድርጅት ባለቤት ነች፡፡ የራሷ ፈጠራ ብቻ የሆነውን የኬክ ጣዕም ለመቅመስ ደንበኞቿ ከሩቅ ቦታ ወደ ትንሿ መደብር ይመጣሉ። አንድ ወጣት ልጅ ዝነኛ ኬኳን ከበላ በኋላ ከተማው ውስጥ ሞቶ ስለተገኘ ለመላው ማህበረሰብ እጅግ አስደንጋጭ ነገር ሆነ። በቅርቡ በኃላፊነት የተሾመው የፖሊስ አዛዥ ለጉዳዩ አስቸኳይ ዕልባት ለመስጠት ቃል ተብቷል፡፡ ጂንጀር ልትረዳው ብትፈልግም፣ እሱ ግን ድርጅቷ ውስጥ ተቀጣሪ የሆነን ሰው በግድያ ወንጀል ከሰሰ፡፡ እሷ ደግሞ ወጣቱ የፖሊስ አዛዥ ስለግድያ ወንጀሉ የደረሰበትን ድምዳሜ ስላለመነችበት ተቃወመችና ወንጀለኛውን ለማወቅ በምስጢር ራሷ ወንጀሉን መከታተል ጀመረች።”
ርዕስ- ጣፋጭ ጂንጀር መርዝ (Sweet Ginjer Poison)
ደራሲ - ሮበርት በርተን ሮቢንሰን
ተርጓሚ - አምሳሉ ጌታሁን ደርሰህ
ዋጋ 35 ብር
ህትመት - ላንጋኖ ማተሚያ ቤት

Saturday, 22 February 2014 13:19

ወግ

“አንድ ደራሲ በመግቢያው ስለ ጠቅላላ መፅሀፉ ይዘት ሲያብራራ ታላቅ ድግስ አዘጋጅቶ መግቢያ በሩ ላይ በመቆም ውስጥ ስለተዘጋጀው ምግብ ጣፋጭነት እየመሰከረ ወደ ብፌው አቅጣጫ እንደሚመራ ጋባዥ መሆኑ ነው፡፡
ደራሲውም ሆነ ጋባዡ መግቢያው ላይ ቆመው በአንድ አይነት ዜማ ታዳሚው ስለ ድግሱ በቂ ግንዛቤ ኖሮት እንዲገባ በማስረዳት ይደክማሉ፡፡ ይሄን ድግስ ለማዘጋጀት ስለ ተደከመው ድካም፣ በውጤቱም ስለተዘጋጁት አይነቶችም ያብራራሉ።
በውስጥ ስለተደገሰው ድግስ በራፍ ላይ ሆኖ የማብራራት አስፈላጊነት ወይም አላማ የታዳሚውን የመብላት ፍላጎት ማናር /አፒታይዘር/ ጭምር ሳይሆን አይቀርም፡፡ በእኔ እምነት ይህ ተግባር ተጋባዡን ጉጉ ያደርገዋል፡፡
በዚህ መፅሃፍ ውስጥ ስለተካተቱት ታሪኮች ይዘት ማውራት ካለብኝ ከአትኩሮታቸው በመነሳት እጀምራለሁ፡፡ በአንድ የማህበረሰብ ስብስብ ውስጥ (ሀገር ሊሆን ይችላል) ወሳኝ ሚና ስላላቸው፣ የየነዋሪውም ዋነኛ ግዱ ስለሆኑት ማለትም … ሀይማኖት፣ ፖለቲካና ማህበረ-ባህላዊ እሳቤ ለመዳሰስ ሞክሬያለሁ፡፡”  
ርዕስ - ሕዝብ እና ነፃነት
ደራሲ - ሚካኤል ዲኖ
ዋጋ - 44 ብር

Saturday, 22 February 2014 13:17

ሰሞኑን የወጡ መፃህፍት

ግጥም
“የሰረቀ ሌባ
በካቴና ታስሮ
በፖሊስ ተይዞ
ሲሄድ ወደ ጣቢያ
መንገድ ላይ ያይሃል
ሊሰርቅ የሚሄደው
ዕልፍ-አዕላፍ
ሌባ፡፡”
ርዕስ -
ሲጠይቁ መኖር
(የግጥም ስብሰባ)   
ደራሲ - ደረጀ ምንላርግህ
ዋጋ - 34ብር
ህትመት - አንድነት ፕሪንተርስ

        ከተመሰረተ ስልሳ አምስት አመቱን ያስቆጠረው የተባበሩት መንግስታት ድርጅት፣ አለምአቀፋዊ ተቋምነቱ እና የብዙዎችን ይሁንታ ያገኘበት ሀላፊነቱ በተግባር በሚያከናውነው ስራ አንፃር ሲመዘን ጥያቄ ላይ የወደቀ ድርጅት ነው፡፡ አሁን በሀላፊነት ላይ ያሉት የመንግስታቱ ድርጅት ዋና ፀሀፊ ባን ኪ ሙን የመንግስታቱን ድርጅት የመለወጥ ሀሳብ በተደጋጋሚ ያነሳሉ፡፡ ነገር ግን፣ ድርጅቱን በዋና ፀሀፊነት ካገለገሉ ስምንት ሰዎች ውስጥ አንዱ ብቻ ናቸው ስለ ለውጥ ምንም ተናግረው የማያውቁት፡፡ የተወሰኑ ለውጦች በተለያዩ ጊዜዎች የተደረጉ ቢሆንም፣ በዋና ዋና ጉዳዮች ላይ ግን ምንም አይነት ለውጥ አለመደረጉ ጥያቄዎቹ ከጊዜ ወደ ጊዜ እንዲበረቱ አድርጓል፡፡
በድርጅቱ ላይ የሚነሱ ጥያቄዎች የአባል አገሮቹን ያህል የበዛ እና የተወሳሰበ ቢሆንም፣ በማሻሻያዎቹ ላይ ጥናት ያደረገው ዛክ ቱከር፣ ጥያቄዎቹን በሶስት ዋና ዋና ምድቦች ይከፍላቸዋል። አንደኛው ጥያቄ፡- በመንግስታቱ ድርጅት ውስጥ እንደ ባህል የተያዘውና እንደ አሰራር እየተከተለ ያለው መንገድ፣ ውሁዳን ሊሂቃንን ያካተተው የአባል አገሮች ቡድን የመንግስታቱን ድርጅትም ሆነ የአለም ፖለቲካ አድራጊ እና ፈጣሪ የሚያደርጋቸው ነው፡፡ ሁለተኛው ጥያቄ የሚያተኩረው ደግሞ፡- በመንግስታቱ ድርጅት እንደ አንድ ግብ የተቆጠረው ግሎባላይዜሽን በአባል አገሮች ሉኣላዊነት ላይ እየጋረጠ ያለው ስጋት ላይ ነው፡፡ ድርጅቱ ግጭቶችን በመከላከልም ሆነ ሰብአዊ ቀውስ በሚፈጠርበት ጊዜ ሰብአዊ አገልግሎቶችን በብቃት አይወጣም የሚለው ሶስተኛው ጥያቄ ነው፡፡
በለውጡ ላይ የድርጅቱ ኢኮኖሚያዊና ማህበራዊ ምክር ቤት ትልቅ ቦታ ሊሰጠው ይገባል። በድርጅቱ ቻርተር መሰረት የምክር ቤቱ ሚና ወደ ጥናት እና አማካሪነት ያተኮረ ነው፡፡ ነገር ግን፤ በሚሰራበት የምርምር፣ የባህል፣ የትምህርት፣ የጤና እና ተያያዥ ዘርፎች ላይ ልክ እንደ ፀጥታው ምክር ቤት  በድርጅቱ ስም ውሳኔ ማስተላለፍ የሚችልበት አቅም ሊሰጠውም ይገባል፡፡ ይህ መደረጉ ደግሞ በድርጅቱ ውሳኔ ላይ የብዙሃን ድምፅ እንዲካተት እና በተለይ በአሁኑ ወቅት ክፍተት ያለበት ከሰብአዊ ድጋፎች ጋር የተያያዙ ስራዎች ምላሽ እንዲያገኙ ያስችላል ይላል ዛክ፡፡
የመንግስታቱ ድርጅት ላይ ለውጥ ሲነሳ፣ የብዙዎችን ትኩረት የሚስበው የፀጥታው ምክር ቤት ነው፡፡ ምክር ቤቱ፤ አራቱን የሁለተኛው የአለም ጦርነት አሸናፊዎች ማለትም አሜሪካ፣ እንግሊዝ፣ ፈረንሳይ፣ ሩሲያ እና ቻይና በቋሚ አባልነት  እና በየሁለት አመቱ የሚቀያየሩ አስር ተለዋጭ  አባላትን ይይዛል፡፡ ይህ ምክር ቤት ከሰላም እና ከደህንነት ጉዳዮች ጋር በተያያዘ ከፍተኛው የድርጅቱ ክንፍ በመሆኑ ማዕቀቦችን ይጥላል፣ የሀይል እርምጃዎችን ያፀድቃል ወይንም ይሽራል፡፡ ውሳኔዎችን ተግባራዊ ለማድረግ የዘጠኝ አባላት ድምፅ ሲያስፈልግ የቋሚ አባላቱ ሙሉ የስምምነት ድምፅ ግን የግድ ያስፈልጋል፡፡
የመንግስታቱ ድርጅት የፀጥታው ምክር ቤት ላይ በሚነሱ ጥያቄዎች እና ለማሻሻያ ይረዳሉ በሚል በተጠራ የከፍተኛ ባለሙያዎች ፓናል ሪፖርቱን ለድርጅቱ አቅርቧል፡፡ በፓናሉ ላይ የመንግስታቱ ድርጅት የፀጥታው ምክርቤት የተሰጠውን ሚና መወጣት እንዳቃተው ሪፖርቱ ያሳያል፡፡ በቀዝቃዛው ጦርነት ወቅት ከሞላ ጎደል ሽባ ነበር ማለት ይቻላል፡፡ ከቀዝቃዛው ጦርነት ማብቃት በኋላ የመነቃቃት አዝማሚያ ቢታይም፣ ከተወሰኑ ውጤታማ ስራዎች በስተቀር አንድን አሳሳቢ ጉዳይ ከመከሰቱ በፊት ለመከላከል ወይም ለተፈጠረ ቀውስ መፍትሄ ከማምጣት ይልቅ የሀይል መጠላለፍ እና መቆላለፉ በመጉላቱ፣ ቋሚ የምክር ቤቱ አባሎች ጥቅም ማስጠበቂያ ሆኗል፡፡ በተለያዩ ጊዜዎች ምክር ቤቱን ለማሻሻል የተደረጉ ሙከራዎች በተለይ የምክር ቤቱ አባልነት ላይ ይደረጉ በሚባሉ ማሻሻያዎች ስምምነት ላይ ባለመደረሱ ውድቅ ሲሆኑ ተስተውለዋል፡፡
በፓናሉ ላይ የምክርቤቱን አባላት ቁጥር ከአስራ አምስት ወደ ሀያ አራት በማሳደግ ሁለት ሞዴሎች ለውይይት ቀርበው ነበር፡፡ አንዱ ሞዴል፡- ድምፅን በድምፅ የመሻር መብት የሌላቸው ስድስት አዲስ የቋሚ አባላትን ማካተት ሲሆን፣ ሁለተኛው ሞዴል ደግሞ አዲስ የቋሚ አባላትም ሳይኖሩ በየአራት አመቱ የሚለዋወጥ መቀመጫ ይኑር የሚሉ ናቸው፡፡
የፀጥታው ምክር ቤትን ጉዳይ አስመልክቶ የተሰጡ ብዙ አስተያየቶች አሰራሩ መሻሻል እንዳለበት ይጠቁማሉ፡፡ አምስቱ አገሮች በሞኖፖል ጠቅልለው የያዙት ድምፅን በድምፅ የመሻር መብት በራሱ ከመሰረታዊዎቹ የህግ መርሆዎች ጋር ይጋጫል፡፡ አገሮቹ ውሳኔዎች እንዲያልፉ ወይም እንዲወድቁ ድምፅ የሚሰጡት ከሰብአዊ መብቶች ወይም ከአለም አቀፍ ህግ በመነሳት ሳይሆን፣ ከራሳቸው መንግስት ጥቅም እና ፍላጎት አንፃር ነው። የፀጥታው ምክር ቤት የተቋቋመው አለም አቀፍ ሰላም እና ደህንነትለ ለማስከበር ቢሆንም እያገለገለ ያለው ግን ለየአገሮቹ የኢኮኖሚ ጥቅም እና የጡንቻ ብቃት መለኪያነት ነው፡፡ ምእራባውያኑ በአለም ላይ ዲሞክራሲን የማስፈን እውነተኛ ፍላጎት ካላቸው ሥራው መጀመር ያለበት በመንግስታቱ ድርጅት፣ በተለይም በፀጥታው ምክር ቤት ነው፡፡ ድምፅን በድምፅ የመሻር መብቱ የተሰጠው ፍትሀዊ ባልሆነ መንገድ በመሆኑ ሰላም ማምጣት አልተቻለም፡፡ ይህ አሰራር፣ ክፍፍል እና ብዙ ተቃርኖ ያላቸው ቡድኖች እንዲፈጠሩ እድል ሰጥቷል፡፡ ድምፅን በድምፅ የመሻር መብት በመንግስታቱ ድርጅት ውስጥ ያለ የዲሞክራሲ መርሆችን የሚሸረሽር አሰራር ነው፡፡
በአለም ላይ ያሉ አገሮችና ህዝቦች እጣፈንታ በአምስት አገሮች ፍላጐት እንዲወሰን በመፈቀዱ ምክንያት አለማችን ይሆናሉ ተብለው የማይገመቱ እልቂቶችንና አሳዛኝ ክስተቶችን እንድታስተናግድ ምክንያት ሆኗል፡፡ የሩዋንዳው እልቂት፣ የዳርፉር እና የሶሪያ ሰብአዊ ቀውሶች እንደ ምሳሌ ይጠቀሳሉ። የመንግስታቱ ድርጅት ሩዋንዳ ውስጥ የተከሰተውን የዘር ማጥፋት እልቂት ቀድሞ መከላከል ያልቻለው ድምፅን በድምፅ የመሻር መብት ባላቸው አሜሪካን እና ፈረንሳይ ውሳኔ ነው፡፡ ሁለቱ አገሮች ከየጥቅሞቻቸው በመነሳት፡- አሜሪካ ከገንዘብ ጋር በተያያዘ፣ ፈረንሳይ ደግሞ አጋሮቿን ላለማጣት በሚል የግል ስሌት ውስጥ በመግባታቸው  ነው … ብዙሀን በአደባባይ እንደ በግ የታረዱት። የሲሪላንካው አማፂ ቡድን “ታሚል ታይገርስ” ላይ በመንግስት በኩል ይደርሱ የነበሩ ኢ-ሰብአዊ እርምጃዎችን ለመታደግ በሚል መንግስት ላይ ሊጣል የነበረ ማእቀብ ውድቅ የተደረገው በቻይና ሲሆን መነሻውም ቻይና ከሲሪላንካ መንግስት ጋር ያላትን ወዳጅነት ላለማሻከር ሲባል ነበር፡፡ ሶስተኛ አመቱን የያዘውና  በመንግስታቱ ድርጅት የዘመኑ ከፍተኛ ሰብአዊ ቀውስ የታየበት ነው የሚባለው የሶሪያ ጉዳይም ከዚህ ጨዋታ የዘለለ አይደለም። ለችግሩ መፍትሄ በሚል የቀረበው ረቂቅ የውሳኔ ሀሳብ፣ በቻይና እና በራሺያ ተቀባይነት ባለማግኘቱ ውድቅ እንዲሆን ተደርጓል፡፡ የበሽር አላሳድ መንግስትን የሚደግፉት ቻይና እና ራሺያ፣ የውሳኔ ሀሳቡ መንግስትን ብቻ በመኮነን ተቃዋሚ ሀይሎችን በዝምታ ያለፈው በዚሁ የውሳኔ ሀሳብ በመሆኑ ድምፃቸውን መንፈጋቸውን ይገልፃሉ፡፡ በመንግስታቱ ድርጅት የራሺያ አምባሳደር ቪታሊ ቸርኪን የአገራቸውን ውሳኔ አስመልክቶ ተጠይቀው በሰጡት አስተያየት፣ የውሳኔ ሀሳቡ ሁሉንም ወገኖች በእኩል የሚኮንን ሳይሆን የአላሳድን መንግስት በተናጠል የሚኮንን በመሆኑ አገራቸው ልትቀበለው እንደማትችል ተናግረዋል፡፡
አፍሪካ፤ ጃፓን፤ ህንድ እና የብሪክስ አገሮች የፀጥታው ምክር ቤት አሰራር ላይ የማሻሻያ ለውጥ እንዲደረግ ከሚጎተጉቱ አገሮች እና አካባቢያዊ ድርጅቶች መካከል ይጠቀሳሉ፡፡ አሁን ባለው አሰራር የብዙሀንን ጥቅም ማስከበር እንደማይቻል በተለያዩ ማስረጃዎች አስደግፈው ያቀርባሉ። ድምፅን በድምፅ የመሻር መብት ሙሉ በሙሉ ተግባራዊ እንዳይሆን ቢደረግም ሆነ አገሮች እና አካባቢያዊ ድርጅቶች የመብቱ ተጠቃሚ መሆን ቢችሉ እንኳን፣ የራስን ጥቅም ማስላትን አያስቀርም፤ መጠላለፉን ከማወሳሰብ በስተቀር የሚሉም አሉ፡፡

“...ሀገራችን ፀሐይ ወጥቶ! አሁንማ ፀሐይ ወጥቶልናል። ሆስፒታላችን ከተሰራልን ወዲህ ምን ችግር አለ... ሞትማ እንዲህ በቀላሉም አይደፍረን፡፡ መቼም ነብስ የእግዚሀር ናትና ሲያበቃላት መትረፊያ የላትም እንጂ... እንዲህ በምኑም በምኑም አልጋ መያዝማ ቀርቶአል፡፡ ይኼው አሁን እኔን ከበሽታ ነጻ አውጥቶኛል፡፡ እዚህ ጉያዬ ስር አንድ ሕመም ነበረብኝ... ፍልፍል አድርጎ አውጥቶ ወርውሮልኝ... ይኼው አሁን ነጻ አውጥቶኛል፡፡ ሐኪሙም አየለ የሚባለው ዶ/ር ነው...”
ከላይ ያነበባችሁት በመርሐቤቴ አለም ከተማ እናት ሆስፒታል ያገኘናቸው አባወራ እማኝነት ነው፡፡ መርሐቤቴ በአማራው ክልል የምትገኝ ስትሆን ከአዲስ አበባ በጎጃም መንገድ መካጡሪ ከተማ ሲደረስ ወደ ቀኝ በመታጠፍ ወደ /111/ አንድ መቶ አስራ አንድ ኪሎ ሜትር ጥርጊያ መንገድ ተገብቶ የምትገኝ ነች፡፡ መርሐቤቴ ተራራማ ስትሆን ዠማ የሚባል ወንዝ መሐል ለመሐል የሚጉዋዝባት እጅግ አስደናቂ ተፈጥሮአዊ ውበት ያላት ናት፡፡ በእርግጥ ከስድስት አመት በፊት መንገዱ እንዲህ በዋዛ የማይደፈር ሲሆን አሁን ግን ዳገት ቁልቁለቱ እንዳለ ቢሆንም ጥርጊያው በማማሩ በጥንቃቄ መንዳት እንጂ እንደቀድሞው ሰውን ማሰቃየቱ አብቅቶአል፡፡ እንደሀገሬው ተስፋም ብዙም ሳይቆይ ወደ አስፋልትነት ይቀየራል፡፡ ግራና ቀኙን እያዩ የተራራውን አቀማመጥ፣ ተፈጥሮአዊ ሀብቱን እያደነቁ ከአንዱ ተራራ ወደአንዱ እየተ ዙዋዙዋሩ ሲጉዋዙ ድካሙን ሳያስቡ ከመርሐቤቴ አለም ከተማ ይደርሳሉ፡፡ አለም ከተማ መሐል አደባባይ ላይ አንድ ልጅ የታቀፈ ሰው ሐውልት ያያሉ፡፡ ቀረብ ብለው ሲያጣሩ ምስሉ የሜንሽን ፎር ሜንሽን መስራች የዶ/ር ካርል ሄንዝ ቦም  ነው፡፡ ሜንሽን ፎር ሜንሽን በመርሐቤቴ ከሰራቸው የልማት ስራዎች መካከል እናት ሆስፒታል አንዱ ሲሆን በመሀል ከተማው አደባባይ ላይ የሚገኘው ሐውልት ለአስተዋጽኦው ማስታወሻ ሐገሬው ለመስራቹ ዶ/ር ካርል ያቆመለት ሐውልት ነው፡፡ እኛም ፈልገን የተጉዋዝነው እናት ሆስፒታልን ነውና በመጀመሪያ የሆስፒታሉ ስራ አስኪያጅ የሰጡትን ማብራሪያ ለንባብ እንላለን፡፡
“...እኔ አቶ ደነቀ አየለ እባላለሁ፡፡ በዚህ ሆስፒታል ቀደም ሲል የጤና መኮንን ሆኜ የሰራሁ ስሆን አሁን ደግሞ ስራ አስኪያጅ ነኝ፡፡ በአለም ከተማ እናት ሆስፒታል የተሰራው በሜንሽን ፎር ሜንሽን አማካኝት ሲሆን የመሰረት ድንጋዩ እንደ ኢትዮጵያ አቆጣጠር በ1991 ዓ/ም ተጥሎ በ1996 ዓ/ም በቀድሞው ጠቅላይ ሚኒስትር መለስ ዜናዊ እና በሆስፒታሉ መስራች ዶ/ር ካርል ሄንዝ ቦብ ተመርቆ ህብረተሰቡን በማገልገል ላይ ይገኛል፡፡
ጥ/ ሆስፒታሉ እናት ሆስፒታል የተባለበት ምክንያት ምንድነው?
መ/    የሆስፒታሉ መጠሪያ እናት እንዲሆን የተወሰነው በመስራቹ በዶ/ር ካርል ነው፡፡ ይኼውም የመሰረት ድንጋይ በሚጣልበት ወቅት ለሚሰራው ሆስፒታልም ስም እንዲወጣ ህብረተሰቡ ተነጋግሮ ሁሉም ለምርጫ የሚሆነውን ስም በልቡ ይዞ ነበር ወደስፍራው የተሰበሰበው፡፡ ከወጣው ህብረተሰብ መካከልም ህጻናትም ይገኙ ነበር፡፡ ከህጻናቱ መካከል አንዲት በዝቅተኛ ደረጃ ከሚኖሩ ቤተሰቦች የተወለደች ልጅ በጣም ቆሽሻ፣ በዝንብ ተወርራ በሚያሳዝን ሁኔታ ቆማ ነበር፡፡ ዶ/ር ካርልም ከልጆቹ መካከል ብድግ አድርገው አቅፈው እያዘኑ ከተመለከቱዋት በሁዋላ ስሙዋ ማን እንደሆነ ጠየቁ፡፡ ስሙዋ እናት መሆኑ ሲነገራቸው  ...በቃ ሆስፒታሉ እናት ተብሎአል ብለው ወሰኑ፡፡ በጊዜው ህብረተሰቡ በተለያዩ  ስሞች ላይ ውይይት አድርጎ የነበረ ስለሆነ ለምን በሚል ቅር ቢለውም ውሳኔው በመወሰኑ ሆስፒታሉ እናት ሆስፒታል ተብሎ ተሰይሞአል፡፡ ልጅቱም በሰዎች ለሰዎች ድርጅት ከነቤተሰቦችዋ እየተረዳች ትምህርቷን እንድትቀጥል ተደርጎአል፡፡
ጥ/    ሆስፒታሉ ደረጃው ምንድነው?
መ/    አለም ከተማ እናት ሆስፒታል ደረጃው በመጀመሪያ ደረጃ ወይንም በወረዳ ደረጃ ዲስትሪክት ሆስፒታል ሆኖ የሚሰራ ነው፡፡ ከአካባቢው አቀማመጥ ጋር ተያይዞ ሌላም ተመሳሳይ የጤና ተቋም ባለመኖሩ በአካባቢው የሚኖሩ ወደ 250‚000 /ሁለት መቶ ሀምሳ ሺህ/ የሚሆኑ የህብረተሰብ ክፍሎችን በማገልገል ላይ ነው፡፡ ከሌሎች አጎራባች ክልሎች ወይንም ዞኖች ...ለምሳሌ ከኦሮሞ የሚመጡትንም ተገልጋዮች አካቶ በርካታ ሰዎችን እያገለገለ ይገኛል፡፡ በአሁኑ ወቅት ወደ /158/ አንድ መቶ ሀምሳ ስምንት ሰራተኞችን የያዘ ሲሆን በተለይም ባለሙያዎችን በሚመለከት ከአምስት በላይ ዶክተሮች እና አንድ የጽንስና ማህጸን ሕክምና እስፔሻሊስት ስለሚገኝ ከደረጃው በላይ እየሰራ ነው ማለት ይቻላል፡፡
ዶ/ር አየለ ተሸመ በአለም ከተማ እናት ሆስፒታል የማህጸንና ጽንስ ሐኪምና የሆስ ፒታሉ  ሜዲካል ዳይሬክተር ናቸው፡፡
ጥ/ ዶ/ር አየለ መርሐቤቴን ለስራ ከመመደብ ውጭ አስቀድሞ ያውቁዋታል?
መ/ እኔ ተወላጅነቴም እድገቴም በዚሁ በመርሐቤቴ ነው። አሁን የምኖርበት ቤት ቀደም ሲል ጤና ጣቢያ የነበረና እኔም የተወለድኩበት ማዋለጃ የነበረ ቤት ውስጥ ነው፡፡ ከህክምና ትምህርት ቤት ተመርቄ እንደወጣሁ በጠቅላላ ሐኪምነትም የሰራሁት በዚሁ ሆስፒታል ነው፡፡ ከዚያም ለአራት አመት ያህል ከ2000-2004 እንደገና ስፔሻላይዜሽን ተምሬ በመመለስ የጽንስና ማህጸን ሕክምና እስፔሻሊስት በመሆን በማገልገል ላይ እገኛለሁ፡፡
ጥ/  ምደባው በአጋጣሚ ነው ወይንስ በምርጫ?
መ/ እኔ በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ሕክምና ትምህርት ቤት በጥቁር አንበሳ የመጀመሪያ ዲግሪዬን ስማር የማህጸን መፈንዳት ሪፖርት ሲደረግ ብዙዎች ከመርሐቤቴ የሚመጡ መሆናቸው የሚነገር ነበር፡፡ በጊዜው መንገዱ እጅግ አሳዛኝ እና አስቸጋሪ ስለነበር እንዲሁም የሚፈለገው ሕክምና በጊዜው በአካባቢው ካለው የጤና ጣቢያ አቅም በላይ የሆነ ችግር ስለሆነ ወላዶች በጣም ይሰቃዩ ነበር፡፡ በእርግጥ የሰዎች ለሰዎች ድርጅት አምቡላንስ ይሰጥ ስለነበር ወደአዲስ አበባ እንዲደርሱ የሚደረግ ቢሆንም ከመዘግየት የተነሳ ረጅም ጊዜ በምጥ በመቆየት ሴቶቹ ይጎዱ ነበር፡፡ እናም አንዳንድ ጊዜ የጠዋት ሪፖርት ላይ የማህጸን መፈንዳት ደርሶአል ሲባል ከየት ከመርሐቤቴ ናት? እስከማለት ድረስ መነጋገሪያ መሆኑ በጣም ያሳዝነኝ ነበር፡፡ በእርግጥ ካለው ዘርፈ ብዙ የጤና ችግር ምክንያት አንባቢው በጤና ጣቢያ ደረጃ ባለበት ጊዜም ሶስት እና አራት ሐኪሞች ይመደቡ የነበረ ቢሆንም ሐኪሞቹም በዚህ የመቆየት ፍላጎት ስለሌላቸው እና ከጤና ጣብያው አቅምም ጋር በተያያዘ በተለይም ለወላዶች በቀላሉ የማይፈቱ የጤና ጠንቆች ይገጥሙዋቸው ነበር፡፡ ስለዚህ እኔም ትምህርቴን ልጨርስ እንጂ በዚያ ገጠራማ ቦታ ገብቼ ህብረተሰቡን ማገልገል አለብኝ ብዬ ወሰንኩ፡፡ መጀመሪያ ላይ ምንም እንኩዋን ጠቅላላ ሐኪም ብሆንም የእናቶችን ችግር ስለማውቅ ከሰዎች ለሰዎች ድርጅት ጋር ተነጋግሬ ለሶስት ወር ለወላዶች የድንገተኛ ቀዶ ሕክምና ስልጠና አግኝቼ በማዋለድ ተግባር ላይ እንድሰማራ እራሴን አዘጋጀሁ፡፡ ከዚያም ከኢትዮጵያ የጽንስና ማህጸን ሐኪሞች ማህበር በተገኘው እድል እንደገና ለስድስት ወር ባለሙያዎችን አሰልጥኜ እኔም ስራዬን እዚሁ ቀጠልኩ፡፡
ጥ/ በገጠር ሆስፒታል ውስጥ እስፔሻሊስት ይመደባልን?
መ/ በጀት ስለሌለ የገጠር ሆስፒታል ውስጥ እስፔሻሊስት አይመደብም፡፡ እናም የጤና ቢሮው እምቢ ቢልም ከዚህ የስራ አመራር ቦርድና ሽማግሌዎች ሄደው በማስፈቀዳቸው እና የእኔም ፍላጎት ስለነበረበት እንድመደብ ተደርጎ በመስራት ላይ ነኝ፡፡
ዶ/ር አየለ ተሸመ በስራቸው ያጋጠማቸውን እንዲህ ሲሉ አውግተዋል፡፡
“...አንዲት ሴት በምጥ ተይዛ በቤቷ ትቆይና ልጇን ትገላገላለች፡፡ ነገር ግን እንግዴ ልጁ እምቢ ስላለ ወደሆስፒታል ያመጡአታል፡፡ ሴትየዋ በሞት እና በህይወት መካከል ነበረች። ስለዚህም እንግዴልጁን ለማውጣት መጀመሪያ የደም ልገሳ እንደሚያስፈልግ ስንነግራቸው እንዴት ተደርጎ የሚል ነገር ተነሳ፡፡ እኛም ምንም ችግር የለውም አልንና... ባለቤቷን...
አንተ ባለቤቷ አይደለህም? አልነው... ነኝ የእርሱ መልስ ነበር፡፡ ታድያ ሚስትህ ከምትሞት አንተ ደም ስጥ... ስንለው  ...አረግ …እኔማ ገበሬ ነኝ ከየት አምጥቼ ነው ለእሷ ደም የምስጥ? መልሱ ነበር፡፡
በመቀጠልም እናትየውን አነጋገርን፡፡
አረግ ...እኔማ ልጄ ብትሞት አልሻም፡፡ ነገር ግን ...እኔ አሮጊት ነኝ ደም ከወዴት አመጣለሁ? ለእኔም አልበቃኝ... መልሳቸው ነበር፡፡ አብረው የነበሩትም ይልቁንም ሳትሞት ይስጡን እና እንውሰድ፡፡ ከሞተች መውሰጃውም አይገኝ ወደሚል ውይይት ገቡ፡፡ እኛም አይናችን እያየ እንዳትሞት ተነጋገርንና ሰዎቹን አስወጥተን ...አንድ ሰራተኛና አንድ አስታማሚ ደም ሰጥተው ህይወቷን አተረፍናት፡፡
ከዚያም ያ ደም የለገሰ ሰውየ ተናደደና ወደሰዎቹ በመሄድ ...ሴትየይቱ  እኮ ሞታለች ...ለምን አስከሬኑን አትወስዱም ሲላቸው... ከተማይቱ እስክትናወጥ ድረስ ኡኡታቸውን አቀለጡት፡፡ በሁዋላም በሉ ዝም በሉ ...እሱዋ ድናለች ሲባል ተደሰቱ፡፡  ከዚያም ወደህብረተሰቡ ሄደው ምስክርነታቸውን ሲሰጡ ለካንስ ይኼም አለ በሚል አሁን ደም የሚለግሱ ሰዎች ማህበር ተቋቁሞአል፡፡ ወደ ሁለት መቶ የሚደርሱ ሰዎች የደም ልገሳ ማህበርተኞች ሆነው ተመዝግበዋል፡፡ ስለዚህም ሰዎቹ የደም አይነታቸው፣ የሚኖሩበት አካባቢ፣ የስልክ ቁጥራቸው ተመዝግቦ የሚገኝ ስለሆነ አስፈላጊ በሆነ ጊዜ ካሉበት ድረስ አምቡላንስ እየላክን እንጠራቸዋለን፡፡ ከሰራተኞቹም እኔን ጨምሮ ፈቃደኞች የሆንን በየሶስት ወሩ ደም እንሰጣለን። እናት ሆስፒታል የደም ባንክ ባይኖረውም አስፈላጊው የላቦራቶሪ ስራ እየተሰራ ለተጠቃሚዎች ደም ይሰጣል፡፡ በእርግጥ ከአዲስ አበባም ደም ባንክ የተቻለውን ያህል ደም ቢሰጠንም በቂ ስለማይሆን ከህብረተሰቡ የሚደረግልን እገዛ ችግሩን አስቀርቶልናል፡፡ ይህም ጥሩ ተሞክሮ ስለሆነ ለሌሎች እንደምሳሌ የሚነሳ ሆኖአል፡፡
ይቀጥላል፡፡

“የተሳፋሪው ፍላጎት የሆነ መሬት ላይ ማረፍ ብቻ  ነበር”
በሃዋሳ ከተማ በተለምዶ ኬሮ ሰፈር እየተባለ በሚጠራው አካባቢ ተወልዶ ያደገው ወጣት ምህረቱ ገብሬ፣ የመጀመሪያ ደረጃ ትምህርቱን በቀድሞው ሀዋሳ ኮምቦኒ የመጀመርያ ደረጃ ት/ቤት ነው የተከታተለው። የሁለተኛ ደረጃ ማጠናቀቂያና የመሰናዶ ትምህርቱንም በቅዱስ ዳንኤል ኮምቦኒ የሁለተኛ ደረጃና የመሰናዶ ት/ቤት አጠናቋል። ከሃዋሳ ዩኒቨርሲቲ በ2001 ዓ.ም በሲቪል ምህንድስና የመጀመሪያ ዲግሪውን ካገኘ በኋላም፤ እስከ 2004 ዓ.ም ድረስ በዩኒቨርሲቲው ውስጥ በመምህርነት አገልግሏል፡፡ በመቀጠልም ነጻ የትምህርት ዕድል በማግኘት፣ ወደ ጣሊያን አምርቶ የሁለተኛ ዲግሪ ትምህርቱን በመከታተል ላይ ይገኛል፡፡
በቅርቡ ለእረፍት ወደ አገሩ የመጣውና በሃዋሳ ቆይቶ ወደ ጣሊያን ለመመለስ አውሮፕላን የተሳፈረው ምህረቱ፣ ባለፈው ሰኞ በረዳት አብራሪው ተጠልፎ ጄኔቭ እንዲያርፍ በተደረገው የኢትዮጵያ አየር መንገድ ቦይንግ 767 አውሮፕላን ውስጥ ከነበሩት 200 ገደማ ተሳፋሪዎች ውስጥ አንዱ ነበር፡፡ በአሁኑ ወቅት በጣሊያን የሚገኘው ምህረቱ፣ የጠለፋውን አጋጣሚ በተመለከተ ጋዜጠኛ አንተነህ  ይግዛው በኢ-ሜይል ለላከለት ጥያቄዎች የሰጠውን ምላሽ  እንደሚከተለው አጠናቅረን አቅርበነዋል፡፡  

የጉዞው አጀማመር ምን ይመስል ነበር?
አርፍዶ ወደ አውሮፕላን ጣቢያ መምጣት የሚያደርሰውን ጣጣ ስለማውቀው፣ አውሮፕላኑ ከሚነሳበት 50 ደቂቃ ያህል ቀድሜ ነበር የተገኘሁት፡፡ ከምሽቱ አራት ሰዓት አካባቢ ማለት ነው፡፡ ያው ጉዞው ሲጀመር እንደሌላው ጊዜ ሁሉ ስርአቱን የጠበቀና ሰላማዊ ነበር።  አውሮፕላኑ ከበራራ ሰዓቱ ሰባት ደቂቃ ያህል ዘግይቶ ነበር የተነሳው።
አውሮፕላኑ ውስጥ አቀማመጥህ እንዴት ነበር? የት አካባቢ ነው የተቀመጥከው?
የመቀመጫዬ ቁጥር 27F ነበር። የተሳፈርንበት ቦይንግ 767 በርዝመቱ ትይዩ 7 የመቀመጫ መደዳዎች አሉት። ሁለት ሁለት መደዳዎች በሁለቱም ጥጎች እና ሶስት መደዳዎች መሃል ላይ። እኔ የተቀመጥኩት ከመሃል ሶስቱ መደዳዎች የመሃለኛዋ ወንበር ላይ ነበር። ከበስተግራዬ ያለችው ወንበር ላይ የተቀመጡት ሪካርዶ የተባሉ የ85 አመት የዕድሜ ባለጸጋ ጣሊያናዊ ነበሩ፡፡ በቀኜ በኩል እንዲሁ በግምት በስድሳዎቹ ዕድሜ ክልል ውስጥ የሚገኙ ሌላ ጣሊያናዊ ተቀምጠው ነበር፡፡ ተዋውቀን ነበር፣ አሁን ግን ዘንግቼዋለሁ። ኢትዮጵያን ተዟዙረው እንደጎበኟት እያጫወቱኝ ነው ጉዞውን የጀመርነው፡፡
ጉዞውስ  እንዴት ነበር?
እንደማስታውሰው ጉዞው ሲጀመር ሰላማዊ ነበር። ከፓይለቱ ጋርም ግንኙነት (ኮሙኒኬሽን)  ነበረን፡፡ እኔ ድካም ስለተሰማኝ ወዲያው አሸለብኩ፡፡ በረራው ከተጀመረ በግምት ከ1 ሰዓት በኋላ የሱዳን አየር ክልል ውስጥ ይሆናል ብዬ እገምታለሁ. . . መብራት ሲበራ ከእንቅልፌ ነቃሁ፡፡ የምግብ ሰዓት መድረሱ ገብቶኛል። ወደ ፊት አሻግሬ ሳይ ሆስተሶቹ እያስተናገዱ ከእኔ ፊት 4ኛ ይሁን 5ኛ ረድፍ ደርሰዋል። ሁሉም ተዘገጃጅቶ እየተጠባበቀ ነበር። በዚህ መሃል የፕሌኑ ፍጥነት ሲጨምር ይታወቀኛል፡፡ ከፍታዉም ሲጨምር በጆሮዬ ላይ በሚሰማኝ ስሜት አስተዋልኩ። በተሳፋሪዎች ፊት ላይ የመረበሽ ስሜት ሲፈጠር አየሁ። እኛ  ኢኮኖሚ ክላስ ስለነበርን ከፊት ምን እየተካሄደ እንደነበር አላየንም። በኋላ ስሰማ ከፊት የነበሩትም የቢዝነስ ክላስ ተሳፋሪዎች ምንም መረጃ አልነበራቸውም፡፡
ከዚያም በድምጽ ማጉያው የሆነ ድምጽ ተሰማ፡፡ የረዳት አብራሪው ድምጽ ነበር።
“ተሳፋሪዎች ከ 12 ደቂቃዎች በኋላ ሚላን እናርፋለን” አለ ረዳት አብራሪው፡፡ ጥቂት ቆይቶም፣ “ስለተፈጠሩ አንዳንድ መጉላላቶች ይቅርታ እንጠይቃለን” ሲል አከለ-በእንግሊዝኛና በአማርኛ ቋንቋ። የረዳት አብራሪውን ንግግር ተከትሎ የተወሰኑ ተሳፋሪዎች ማጉረምረም ጀመሩ፡፡ አንዳንዶችም ጮክ ብለው ሲያወሩ ይሰሙ ነበር፡፡ ከኔ በስተግራ በኩል ሶስት አራት መደዳዎችን አልፎ ከፊቴ ተቀምጦ የነበረ አንድ ወፍራም ሰው፣ በጣሊያንኛ ቆጣ ብሎ እየጮኸ ተናገረ - “መጀመሪያ ሚላን ሳይሆን ሮም ነው ማረፍ ያለብን ፣ ወደ ሮም ውሰዱን!” በማለት። ሌሎችም የሰውየውን ሃሳብ ደገፉ፡፡ ምክንያቱም አብዛኛው ተሳፋሪ ወደ ሮም ነበር የሚጓዘው። ረዳት አብራሪው ሚላን ላይ እንደምናርፍ መናገሩ ብዙዎችን አበሳጭቶ ነበር፡፡  
እውነቱን ለመናገር፣ እኔ ግን ሚላን እንደምናርፍ ስሰማ ደስ ብሎኝ ነበር፡፡ ምክንያቱም እኔ ሚላን ወራጅ ነኝ፡፡ ረዳት አብራሪው የነገረን አስራ ሁለቱ ደቂቃዎች እየተገባደዱ መሆናቸው ሲገባኝ፣ ከአውሮፕላኑ ለመውረድ መዘገጃጀትና ጓዜን መሸካከፍ ሁሉ ጀመርኩ። ሆኖም  አስራ ሁለቱ ደቂቃዎች አልፈውም አውሮፕላኑ አላረፈም፡፡ ካሁን አሁን ሚላን አውሮፕላን ማረፊያ ደረስን እያልን ስንጠባበቅ፣ ሌላ አስራ ሁለት ደቂቃዎች አለፉ፡፡ አሁንም ሌላ አስራ ሁለት ደቂቃዎች---
ተሳፋሪው ሁሉ ግራ በመጋባት ሰዓቱን ደጋግሞ መመልከትና እርስ በርስ በጥርጣሬ መተያየት ጀመረ። ከአስራ ሁለት ደቂቃዎች በኋላ ሚላን ላይ ያርፋል የተባለው አውሮፕላን፣ ከአንድ ሰዓት ተኩል በላይ በአየር ላይ ቆየ፡፡ የሚገርመው ያን ያህል ጊዜ አየር ላይ መቆየቱ ብቻ አይደለም፡፡ አበራረሩ የተለየ ነበር፡፡ አንዴ ፍጥነቱን ጨምሮ ይከንፋል፣ ከዚያ ደግሞ ፍጥነቱን ይቀንስና ተረጋግቶ ይበራል፡፡ እንደገና ይፈጥናል፣ እንደገና ይረጋጋል፡፡ ግራ ገብቶን እያለን፣ ከመቅጽበት አውሮፕላኑ ማረፊያው ላይ ደርሶ ማኮብኮብ ጀመረ፡፡ ያንን ያህል ግዙፍ አውሮፕላን፣ በዚያች ጠባብ ቦታ ላይ ያለችግር ማሳረፍ መቻሉ፣ የረዳት አብራሪውን ብቃት ያሳያል፡፡ ለማንኛውም አውሮፕላኑ በሰላም አረፈና እኛም እፎይ አልን፡፡
አውሮፕላኑ ካረፈ በኋላ የተሳፋሪዎች ስሜት ምን ይመስል ነበር?
የሚገርመው ነገር፣ አውሮፕላኑ እንዳረፈ በተሳፋሪው ፊት ላይ ከታየው ደስታና እፎይታ በተጨማሪ፣ ተሳፋሪው ለረዳት አብራሪው የሰጠው አድናቆት ነበር፡፡ አብዛኛው ተሳፋሪ ስለረዳት አብራሪው ችሎታ ነበር ተደንቆ የሚያወራው፡፡ በከፍተኛ የአድናቆት ስሜት ተውጠው፣ ለረዳት አብራሪው ያላቸውን አድናቆት በጭብጨባና በፉጨት የገለፁም ነበሩ፡፡ እኔም በደመነፍስ ሳጨበጭብ ነበር፡፡ ሚላን ምድር ላይ በሰላም እንዲያሳርፈኝ ለፈጣሪዬ ያደረስኩትን ጸሎት የማውቀው እኔ ነኝ፡፡
ሚላን እንዳረፋችሁ ነበር የምታውቁት ማለት ነው?
የሚገርመው እኮ እሱ ነው!... አውሮፕላኑ መሬት ከነካ በኋላ ሁሉ፣ ተሳፋሪው በሙሉ ጣሊያን ሚላን እንዳረፈ ነበር የሚያውቀው፡፡ ሚላን እንደምናርፍ ነው ረዳት አብራሪው የነገረን፡፡ ትኬት ከፍለን የተሳፈርነውም ወደ ጣሊያን እንጂ ወደ ስዊዘርላንድ ለመሄድ አልነበረም። በዚህ ቅጽበት ጄኔቭ የምትባል ከተማ በምን ተአምር እንሄዳለን ብለን እናስብ?
ጄኔቭ መሆናችሁን ያወቃችሁት እንዴት ነው?
አውሮፕላኑ በሰላም ካረፈ በኋላ ተሳፋሪው ከጭንቀቱ ተገላግሎ መረጋጋት ጀመረ፡፡ አንዳንዶች ሞባይል ስልኮቻቸውን አውጥተው መነካካት ያዙ። በሞባይላቸው የኢንተርኔት መስመር በመጠቀም ጎግል ማፕ የተሰኘውን የአገራትና የከተሞች ካርታ የሚያሳይ ድረገጽ፣ ጂ ፒ ኤስ ከሚባለው አቅጣጫ ጠቋሚ ቴክኖሎጂ ጋር አያይዘው ሲመለከቱ፣ ፊታቸው ላይ ድንገተኛ መደናገር ሲፈጠር አየሁ፡፡ አንዱ ተሳፋሪ ሞባይሉ ላይ ያየውን መረጃ በመጠራጠር፣ የሌላኛውን ሞባይል ማየት ጀመረ፡፡ “የት ነው ያለነው?” ለሚለው ጥያቄ እርግጠኛ የሆነ መልስ የሚሰጥ ጠፋ፡፡ ግማሹ “ ኦስትሪያ ነን!” ሲል፣ ገሚሱ “የለም ፈረንሳይ ነን!” ብሎ ይመልሳል፡፡ አንዳንዱ “ጀርመን ውስጥ ነው የምንገኘው!” ይላል፡፡ ሌላው “ስዊዘርላንድ ጄኔቭ ነው ያረፍነው!” እያለ ይናገራል፡፡ ጭንቀትና ውጥረት የፈጠረው መደናገር ሊሆን እንደሚችል ያሰብኩት በኋላ ነው፡፡
 ጄኔቭ ማረፋችሁንና አውሮፕላኑ መጠለፉን ያወቃችሁት እንዴት ነበር?
እያንዳንዱ ተሳፋሪ አውሮፕላኑ ያረፈበትን አገርና ከተማ በተመለከተ የየራሱን መላምት እየሰነዘረ ግራ ተጋብቶ ጥቂት ደቂቃዎች አለፉ፡፡ በዚህ መሃል ነው፣ ድንገት የአውሮፕላኑን ዋና አብራሪ ድምጽ የሰማነው። በረራው ከተጀመረ አንስቶ የዋና አብራሪውን ድምጽ ስንሰማ ለመጀመሪያ ጊዜያችን ነበር፡፡ ዋና አብራሪው በጣሊያንኛ ቋንቋ ነበር የሚያወሩት፡፡ በጣሊያን ቆይታዬ የቀሰምኳት ቋንቋ ብዙም የምታወላዳ አልነበረችምና፣ ደቂቃዎችን ከፈጀው የአብራሪው ንግግር የተወሰነችዋን ተረድቼ፣ ቀሪውን ከጎኔ ከተቀመጡት ጣሊያናውያን ጠይቄ ለመረዳት ሞከርኩ፡፡
አብራሪው  ወደመጸዳጃ ቤት ሲወጡ ረዳት አብራሪው በር እንደዘጋባቸው፤ አውሮፕላኑን ለሰዓታት ሲያበር የቆየው ረዳት አብራሪው እንደነበር፤ አውሮፕላኑ ያረፈው ጄኔቭ መሆኑን፤ በተፈጠረው ነገር ማዘናቸውን መግለጻቸውን እንዲሁም እያንዳንዱ ተሳፋሪ የስዊዘርላንድ ፖሊሶች ለሚያደርጉት ምርመራ ተገቢውን ትብብር እንዲያደርግ ጥሪ ማስተላለፋቸውን ነገሩኝ፡፡ ተሳፋሪው ስለ ጠለፋው ያወቀው በዚህ ጊዜ ነው፡፡
ተጠልፋችሁ ያላሰባችሁት ቦታ እንዳረፋችሁ ስታውቁ ምን ተሰማችሁ?
እውነቱን ለመናገር በወቅቱ የሁሉም ተሳፋሪ ጸሎትና ምኞት በረራው በሰላም መጠናቀቁና አውሮፕላኑ አደጋ ሳያጋጥመው ማረፉ ብቻ ነበር፡፡ የተሳፋሪው ፍላጎት የትም ይሁን የት፣ ብቻ የሆነ መሬት ላይ ማረፍና ከጭንቀት መገላገል ነበር፡፡ አስበው እስኪ… ከአብራሪውም ሆነ ከሆስተሶቹ ጋር ምንም አይነት ግንኙነት በሌለበት አደናጋሪ ሁኔታ ውስጥ ነው ለሰዓታት የበረርነው፡፡ ከዚያ ደግሞ… ሮም የማረፍ ዕቅዱ ተሰርዞ፣ ከ12 ደቂቃዎች በኋላ ሚላን እንደምናርፍ ድንገት ተነገረን፡፡ ይሁን ብለን ተቀብለን፣ አስራ ሁለቱን ደቂቃ በጉጉት ስንጠባበቅ ደግሞ፣ ለተጨማሪ አንድ ሰዓት ተኩል ያህል ጊዜ በረራው ቀጠለ፡፡ በዚያ ላይ በረራው ጤነኛ አልነበረም፡፡ አንዴ የሚፈጥን፣ ሌላ ጊዜ ደግሞ የሚረጋጋ ምቾት የማይሰጥ በረራ ነበር፡፡
በዚህ ሁኔታ ውስጥ ያለ ተሳፋሪ፣ የትም ቢሆን ማረፍን እንጂ፣ማረፊያ ቦታውን አይመርጥም፡፡ እኔም ሆንኩ ሌሎች ተሳፋሪዎች ጉዳዩን ያወቅነው፣ ጠለፋው ከተጠናቀቀና አውሮፕላኑ ጄኔቭ ውስጥ በሰላም ካረፈ በኋላ ዋና አብራሪው ሲነግሩን በመሆኑ እምብዛም አልተደናገጥንም፡፡  
ከአውሮፕላኑ ስትወርዱ የነበረው ሁኔታ ምን ይመስላል?
አውሮፕላኑ ጄኔቭ ካረፈ በኋላ በግምት ለአንድ ሰአት ያህል በሩ ሳይከፈት ቆሞ ቆየ፡፡ ዋና አብራሪው ሁሉንም ነገር በግልጽ ከነገሩን በኋላ፣ ከእግር ጣታቸው እስከ ራስ ጸጉራቸው የብረት ጭንብል የለበሱ ሰዎች፣ በሩን በርግደው በፍጥነት ወደ ውስጥ ገቡ። አገባባቸውና መላ ሁኔታቸው አክሽን ፊልም የሚሰሩ ነበር የሚመስሉት፡፡ ሁኔታው እጅግ ያስጨንቅ ነበር፡፡ በመካከል አንደኛው ፖሊስ በእጁ በያዛት አነስተኛ የድምጽ ማጉያ ፈረንሳይኛ በሚመስል እንግሊዝኛ መናገር ጀመረ።
“ዚስ ኢዝ ኤ ፖሊስ ኦፔሬሾን። ዶንት ሙቭ!... ፑት ዩር ሃንድስ ኦን ዩር ሄድ!... ዶንት ሜክ ሙቪ ባይ ሞባይል (በሞባይል አትቅረጹ ማለቱ ነው)” ሲል ቀጭን ትዕዛዝ አስተላለፈ፡፡ ሁሉም እጆቹን አናቱ ላይ ጭኖ ድምጹንም አጥፍቶ አቀረቀረ፡፡ ተሳፋሪው በፖሊሶቹ መሪነት አንድ በአንድ ከአውሮፕላኑ እየወረደ፣ ሁለት ሁለት ጊዜ ተበርብሮ ተፈተሸ፡፡
ፍተሻው እንደተጠናቀቀም በትላልቅ ሽንጣም አውቶብሶች እየጫኑ ወደ ተርሚናሉ ወሰዱን፡፡ ተርሚናሉ ላይ ስንደርስ የሚገርም አቀባበል ተደረገልን፡፡ የምንበላው ቁርስና ሻይ ቡና እንዲሁም ለብርዱ ብርድልብስ ተዘጋጅቶ ጠበቀን፡፡ የህክምና ባለሙያዎችና የስነልቦና ባለሙያዎች እርዳታ ሊሰጡን እየተጠባበቁ ነበር፡፡ አስገራሚ አቀባበል ነው የተደረገልን።
ኢትዮጵያውያንስ አላገኛችሁም?
ተርሚናሉ ዉስጥ ገብተን ትንሽ እንደቆየን አንድ ኢትዮጵያዊ ወደ እኛ ሲመጣ ተመለከትን፡፡ ለጊዜው ስሙ ትዝ አይለኝም። ከኢትዮጵያ ኤምባሲ እንደመጣ ነገረንና ስለሁኔታው ጠየቀን። “አይዟችሁ!... ደርሰንላችኋል!...” የሚል መንፈስ ያለው ማበረታቻ ሰጠን፡፡ ከዚያም የግል ሞባይሉን ከኪሱ አውጥቶ አገር ቤት ያሉ ቤተሰቦቻችን ጋ ደውለን ደህንነታችንን እንድናረጋግጥ ራሱ እየደወለ ያገናኘን ጀመር፡፡   
በዚህ ጊዜ ነው፣ በስዊዘርላንድ የኢትዮጵያ አምባሳደር የመጡት፡፡ በአውሮፕላኑ ውስጥ የነበርን ኢትዮጵያውያንን አነጋግረው አረጋጉን፡፡ በስተመጨረሻም ከተርሚናሉ እንዲወጡ ስለታዘዙ የማስታወሻ ፎቶግራፍ አብረውን ተነሱና ጉዳያችንን በቅርብ እንደሚከታተሉ ነግረውን አበረታቱንና ሄዱ፡፡ ሌሎች ሁለት የኤምባሲው ባልደረቦችም፣የሚፈቀድላቸው ቦታዎች ላይ ሁሉ እየተገኙ ድጋፍ በማድረግ እስከመጨረሻው አብረዉን ነበሩ።
በእለቱ ስለተከሰተው ሁኔታ ምን ትላለህ?
እናቴ እንደነገረችኝ፣ በህፃንነቴ የወራት ዕድሜ ላይ እያለሁ፣ የሆነ ቀን ከታላቅ ወንድሜ መላኩ ገብሬ ጋር ከጎማ ላስቲክ የተሰራ አልጋ ላይ ተኝቼ ነበር። ቡና ስታፈላ ምንጊዜም ዕጣን ማጨስ እማትዘነጋው እናታችን፣ ያጨሰችዉን እጣን እኛ የተኛንበት አልጋ አጠገብ አስቀምጣው ኖሮ፣ እሷ ጎረቤት ደርሳ ስትመለስ ቤቱ በጭስ ተሸፍኖ ጨልሞ ጠበቃት። ጩኸቷን ለቀቀችው። ጩኸት ሰምቶ የመጣ ጎረቤት ነው አሉ ፈልጎ አግኝቶኝ በመስኮት ወደ ውጭ የወረወረኝ። ምህረቱ የተባልኩትም በዚያ ምክንያት ነው። እንዳጋጣሚ እሳቱ ቀድሞ የተያያዘው ወንድሜ በተኛበት በኩል ስለነበር እሱን ማትረፍ አልተቻለም።
የፈጣሪ ምህረት ዛሬም አልተለየኝም፡፡ በአውሮፕላኑ ላይ ሊደርስ ከሚችለው አሰቃቂ አደጋ አትርፎኛል። እንደትላንትናው ሁሉ ነገዬም በፈጣሪ እጅ እንደሆነች አምናለሁ። እርሱ ይሁን ያለው ሁሉ መልካም ነው። ቸርነቱ አይለየኝና ፍቃዱ ሆኖ ለነገ ካበቃኝ ለልጆቼ የምነግረው ተጨማሪ ታሪክ አግኝቻለሁ።
ደህና ነኝ እንኳን ብላት የማታምነኝ እናቴ ብርሃነማርያም ኪአን፣ እጮኛዬ ዮዲት ቦርሳሞን፣ ወንድሞቼን፣ ብቸኛዋን እህቴን፣ አክስቶቼን ከነቤተሰቦቻቸው፣ ጓደኞቼን፣ስለደህንነቴ የሚጨነቁልኝን ሁሉ ደህና መሆኔን ንገርልኝ። ከሁሉ አስቀድሞ ስለሆነውም ስለሚሆነዉም ክብር ሁሉ የእርሱ ነውና ፈጣሪ የሚገባዉን ክብር እና ምስጋና ይውሰድ።

Saturday, 22 February 2014 13:00

የቀልድ - ጥግ

ትንሽ     ስለ ቀልድ

ቀልድ መቼና እንዴት መጠቀም አለብን ብሎ መጠየቅ ያባት ነው፡፡ ቀልድ በመደበኛም ሆነ በኢመደበኛ ንግግር ውስጥ መሠረታዊ ግብዓት ሆኖ ያገለግላል፡፡ ቀልድ ቅመም ነው፡፡ ወጥ በቅመም እንደሚጣፍጥ ሁሉ በጥንቃቄ መመረጥ፣ መመጠንና በትክክለኛው ሰዓት መጨመር ይኖርበታል፡፡ ቀልድ በትክክል ከተመጠነና ከተጨመረ በብርቱ ጥንቃቄ በበቃ ባለሙያ የተነገረውን ዲስኩር እንኳ የበለጠ አመርቂና ለታዳሚው እጅግ የሚጥም ያደርገዋል፡፡
ጆርጅ ጄሰል የተባለ ፀሐፊ፣ “ጥሩ ንግግር ልክ እንደጥሩ ካልሢ፣ ካልሢው በተሰራበት ጨርቅ ዓይነት ይወሰናል” ይላል፡፡ (የቻይናን አቃጣይ ካልሲዎች ልብ ይሏል) የቀልድ ጥግ የሚለው የአምድ-ሩብ፤ ታላላቅ ሰዎች፣ ነጋዴዎች፣ ወጣቶች፣ የጥበብ ሰዎች፤ በንግግር፣ በውይይት፣ በስብሰባ መግቢያና ሌሎች የዕለት ተዕለት የንግግር እንቅስቃሴዎቻቸው ውስጥ፤ ትኩስ የቀልድ ምንጭ እንዲሆን የታሰበና የተዘጋጀ ነው። ቀልዶቹ በዘርፍ የተከፋፈሉ ስለሆነ በአጫጭር ጭውውቶች፣ ገጠመኞች፣ ተረቦች፣ ውጋውጎች /witticisms/፣ የነገር አዋቂዎች አባባሎች፣ ተረቶችና የአንዳንድ ሀሳቦች ትርጓሜዎች ወዘተ እየተመረጠ የሚቀርብበት ነው፡፡
በመሰረቱ ቀልድ መጠቀም ያለብን አንድን መልዕክት ፅኑ ነጥብ ለማጠንከር ስንሻ ወይም የተደበረና የተኮሳተረን ታዳሚ ላላ ለማድረግ ስናስብ፤ አሊያም የከረረና የመረረ ስሜቱን በተለየ አቅጣጫ ለመቃኘት ስንፈልግ ነው፡፡
ቀልድ ሌላውን ሰው ወይም ታዳሚ ለማጥቃት የምንጠቀምበት መሆን የለበትም፡፡ ስለዚህ ከመጠቀማችን በፊት የታዳሚው ምላሽ ምን ይሆናል? ታዳሚው  ምን ይሰማዋል? ብሎ ማሰብ መልካም ነው፡፡ ለማረጋገጥ በራሳችን የቅርብ ሰው ላይ ሞክረን የሚያስከፋው መሆኑን ማጤን ይገባል፡፡
ቀልድ ለዛ የሚኖረው በቦታው ሲቀርብ፣ በሰዓቱ ስንገለገልበት ነው፡፡ ቀልድ በኮስታራ ንግግር ውስጥ ጣልቃ አስገብተን ከምንጠቀምበት ሰዎች ጀምሮ፤ ለመዝናኛ እንደማሺንገን የሚተኩሱ፣ እንደተልባ የሚንጣጡ ኮሜዲያኖች እስከሚጠቀሙበት ድረስ፤ የተለያየ የመገልገያ መንገድ አለው፡፡ ሆኖም ብዙዎች በዚህ ጉዳይ ላይ የተመራመሩ ፀሐፍት ቀልዶች አንድ ላይ እንደጥይት ዝናር ከሚደረደሩ ከቁምነገር ንግግሮች መካከል ጣልቃ ቢገቡ እንደለዘዘ ቆሎ ጥርስ ከማስቸገር ይድናሉ ይላሉ፡፡
እኛም ይህንን መንፈስ በማጠንከር የተወሰኑ ቀልዶችን ብቻ በየጊዜው እናቀርብላችኋለን፡፡
የቀልዶቹ ዘርፎች ለምሳሌ አንድ ሳምንት በሰካራሞችና በአካል ዙሪያ፣ በሌላ ሳምንት በዶክተሮችና በሕክምና ዙሪያ፣ ቀጥሎ በባንክና በባንከሮች ዙሪያ፣ ከዚያ በነጋዴዎችና በንግድ ዙሪያ እንቀጥላለን፡፡ እናንተም ያጋጠማችሁን የሰማችኋቸውን ብትልኩልን ደስ ይለናል፡፡ ሣምንት እንጀምርላችኋለን፡፡

“ቱሪዝም አሁንም ገና ጨቅላ ነው”
የአገሪቱን ቱሪዝም ምቅር ቤት የሚመሩት ጠቅላይ ሚኒስትሩ ናቸው
አስጐብኚ ምንም ነገር አላውቅም ማለት የለበትም
ባለፈው የጥምቀት በዓል ሰሞን በጎንደር ከተከናወኑት ጉዳዮች አንዱ የጎንደር እህት ከተማ በሆነችው የፈረንሳይዋ ቬንሰን ከተማ ሁለገብ እድሳት ተደርጎለት የተጠናቀቀውን የ“ራስ ግንብ”ን ማስመረቅ ነበር፡፡
ግንቡ ራስ ሚካኤል ስሁልን ጨምሮ በርካታ የጎንደር ነገስታት ራሶች መኖርያ ስለነበር ነው፡፡ “ራስ ግንብ” የተባለው፡፡
የአዲስ አድማስ ጋዜጠኛ ናፍቆት ዮሴፍ፣ ለ20 ዓመታት የፋሲል አብያተ-መንግስትን በማስጎብኘት እውቅናና አድናቆትን ካተረፉት
የቱሪዝም ከፍተኛ ኤክስፐርት አቶ ጌትነት ይግዛው ንጉሴ ጋር በጐንደር የቱሪዝም እንቅስቃሴ፣ በታሪካዊ ቅርሶች እድሳት፣
በአስጎብኝነት ህይወታቸው፣ እንዲሁም
በቱሪዝም ኢንዱስትሪና ተያያዥ
ጉዳዮች ዙርያ
ቃለምልልስ አድርጋለች፡፡  

ወደ ፌደራል ባህልና ቱሪዝም ሚኒስቴር ከመምጣትዎ በፊት የአፄ ፋሲል አብያተ መንግስትን ለ20 ዓመታት እንዳስጎበኙ ሰምቻለሁ፡፡ እስቲ ስለዚህ ጉዳይ ያጫውቱኝ …
ዌል! ይሄ ረጅም ጊዜ ነው፡፡ ለ 21 ዓመታት የቱሪስት ጋይድ ነበርኩ፤ የጎንደር አካባቢ ሲኒየር ጋይድ ሆኜ ሰርቻለሁ፡፡ ከዛ በኋላ የጎንደር ዓለም አቀፍ ቅርስ አስተዳደር (የአብያተ መንግስታት አስተዳደር) ማናጀር ሆንኩኝ፡፡ የዩኔስኮም ተጠሪ (ፎካል ፐርሰን) ሆኜ ሰርቻለሁ፡፡ የጎንደር ቅርሶች በዓለም አቀፍ ደረጃ የተመዘገቡ በመሆናቸው፣ አሁን እኔ ስራዬን ወደ ፌደራል ባህልና ቱሪዝም በመቀየር የዛሬ አንድ ዓመት ከአምስት ወር አካባቢ ጀምሮ የቱሪዝም ከፍተኛ ኤክስፐርት ሆኜ እየሰራሁ ነው፡፡
ጎንደርን ለመጎብኘት እጅግ በርካታ ቱሪስቶች ይመጣሉ፤ አንዱ ሲሄድ ሌላው እየተተካ በቀን ለብዙ ጎብኚዎች ገለፃ ማድረግ ይኖርብዎታል፡፡ አድካሚነቱ ምን ያህል ነበር?
የማስጎብኘት ሥራ የዲፕሎማሲ ስራ እንደመሆኑ የአገርን ታሪክ፣ የአገርና ህዝብን ባህል፣ የአገርን ኢኮኖሚና ፖለቲካ እያገናዘቡ፣ ህዝብንና አገርን ማዕከል በማድረግ ገለፃ የሚደረግበት ነው፡፡ እንዳልሽው የተለያየ ዓይነት ቱሪስት ነው የሚመጣው፤ ከአገር ውስጥም ከውጭም ማለቴ ነው፡፡ እጅግ በርካት የሆኑ ሰዎችን አግኝቻለሁ። ለምሳሌ የአገር መሪዎች፣ በርካታ የጥናትና ምርምር ስራ የሚሰሩ ባለሙያዎች፣ ለመዝናናትና አዲስ ተመክሮ ለመቅሰም የሚጓዙና መሰል ሰዎችን አግኝቻለሁ፡፡ ምክንያቱም ሁለት አስርት ዓመታት ቀላል አይደሉም፡፡ እንደውም ዝም ብዬ ሳስበው የያኔው ስራዬ አሁን ካለሁበት ስራ አንፃር ሲታይ እጅግ ውስብስብ ነበር፡፡ ምክንያቱም በቱሪዝም ህግ መሰረት አንድ አስጎብኚ “አላውቅም” አይልም፡፡ ስለዚህ የምትጠየቂውን ሁሉ መመለስ ይጠበቅብሻል፡፡ ስትመልሺ ታዲያ ታሪክሽን እንዳታዛቢ ከፍተኛ ጥንቃቄ ማድረግ አለብሽ፡፡ ምክንያቱም አሁን በዓለማችን ውስጥ ከፍተኛ የታሪክ ሽሚያ አለ፡፡ ሃይማኖትን፣ ዘርንና ቀለምን ሳታይ ለሁሉም እኩል መስተንግዶ መስጠት ግዴታሽ ነዉ። ከዚህ አንፃር ሳየው በጣም የተወሳሰበና አድካሚ ነበር፤ ሆኖም ኃላፊነቴን በአግባቡ ተወጥቻለሁ ብዬ አምናለሁ፡፡
የትምህርት ዝግጅትዎ ከቱሪዝም ሙያ ጋር የተያያዘ ነው?
የትምህርት ዝግጅቴ ከቱሪዝምና ከቅርስ አስተዳደር የወጣ አይደለም፡፡ ከሰርተፍኬት ጀምሮ እስከ ማስተርስ ዲግሪ የሰራሁት ከቱሪዝምና ከቅርስ አስተዳደር እስከ ሄሪቴጅ ማኔጅመንት ድረስ ነው። ለምሳሌ ማስተርሴን የሰራሁት በቱሪዝምና ሄሪቴጅ ማኔጅመንት፣ የመጀመሪያ ዲግሪዬ በቱሪዝም ማኔጅመንት፣ ዲፕሎማዬ በእንግሊዝ አገር ከሚገኝ ካምብሪጅ ኮሌጅ በቱሪዝም እና ትራቭል ኤጀንት ማኔጅመንት ሲሆን ሰርተፍኬቴን ያገኘሁት ደግሞ በአገራችን በቱሪዝም ዘርፍ ፈር ቀዳጅ ከሆነው CTTI ቱሪስት ጋይድ በተባለ ዘርፍ ነው፡፡ እንደምታይው ከቱሪዝም አልወጣሁም ማለት ይቻላል፡፡
አንዳንድ ጎብኚዎች በተለይም ከአውሮፓ እና ከሌሎች አህጉራት የሚመጡት የግንቦቹን አሰራር ረቂቅነት ሲመለከቱ እጃችን አለበት በማለት እንደሚሟገቱ ሰምቻለሁ፡፡ እነዚህን ዓይነት ፈታኝ ጥያቄዎች እንዴት ነበር የሚጋፈጧቸው?  
የዓለም ስልጣኔ መጀመሪያ የአፍሪካ አህጉር እንደሆነ በማስረዳት እጀምራለሁ፡፡ ምክንያቱም አገራችን የሰው ዘር መገኛ ሆና በዓለም ከታወቀችበት ጊዜ ጀምሮ እስካሁን በሌላ ዓለም ቀደምት የሰው ዘር ቅሪት አልተገኘም፡፡ ስልጣኔ የሚነሳው ደግሞ ከሰው ልጅ መሆኑ ግልፅ ነው፡፡ ምክንያቱ ደግሞ ሰው የኑሮ ጫናዎቹን ለማቃለል ደፋ ቀና ሲልና ለችግሮቹ መፍትሄ ሲፈልግ ነው ስልጣኔ እና ፈጠራ አብሮ የሚመጣው፡፡ የመጀመሪያው መልሴ ከላይ የገለፅኩት ነው፡፡ አውሮፓውያን የስልጣኔ ምንጭ አውሮፓ ናት ካሉ፣ ያ በእነሱ መልክ ነው የሚሆነው። አሜሪካኖችም እንዲያ ሲሉ በእነሱ መልክና እሳቤ ነው፡፡ ለምን ካልሽኝ … የዛሬ 400 ዓመት የተመሰረተች አገር፣ ከሶስት ሺህ ዓመት በላይ ታሪክ ካላት አገር ጋር እኩል መሆን አትችልም፡፡ የሰው ልጅ እስካለ የኪነ-ህንፃም ሆነ ሌላም ስልጣኔ ይኖራል፡፡ ይህን ሳስረዳቸው የዚያ ጥበብና ስልጣኔ ባለቤት እንደሆንን ያምናሉ፤ የመንፈስ ቅናት አድሮባቸው ካልካዱ በስተቀር ማለቴ ነው፡፡
ከኪነ-ህንፃ ጋር በተያያዘ በተለይ የውጭ ጎብኚዎች ምን ይላሉ? እንዴት ነው ስሜታቸው? ይገርምሻል! አግራሞታቸው ሰፊ ነው፡፡ ጥቁር ህዝብ ቤተ-መንግስት ውስጥ የሚኖርባት የአፍሪካ አገር መሆኗ ይገርማቸዋል፡፡ በእነሱ እምነት ቤተ-መንግስት ውስጥ የሚኖረው አውሮፓዊ ብቻ ነው፤ የታላቋ ብሪታኒያ ነገስታቶች፣ የፈረንሳይ ነገስታቶች ብቻ ይመስሏቸዋል፡፡ ይታይሽ … ከ16ኛው ክ/ዘመን መጀመሪያ አንስቶ እስከ 17ኛው ክ/ዘመን፣ በጎንደርና አካባቢዋ ከፍተኛ ቤተ-መንግስታት ተሰርተው ነበር፤ ስልጣኔውም ነበር፡፡ እንደሚታየው ግንባታው ከኖራ ጋር ተቀላቅሎ ዝም ብሎ የተሰራ ሳይሆን የኪነ-ህንፃ ልዩነቱን ጠብቆ በጥልቅ ፈጠራ የተገነባ ነው እና የኪነ-ህንፃ ጥበብ ያረፈባቸው፣ ገላጭ የሆኑ ህብረ-ህንፃዎች ናቸው፡፡ ይህን በአግራሞትና በመደመም ነው የሚመለከቱት፡፡ ከዚህ አንፃር የሚያነሱት ዘርፈ ብዙ ጥያቄዎች ማባሪያ የላቸውም፡፡
ከ400 ዓመት በላይ እድሜ ያላቸው የፋሲል አብያተ መንግስታት ግንባታዎችን ከአሁኑ ዘመን የኪነ-ጥበብ ህንፃ ጋር ማነፃፀር ይቻላል? እርስዎ ያነፃፅሩ ቢባሉ እንዴት ይገልፁታል?
እንግዲህ ውርስ ሊኖር ይችላል፤ የእውቀትና የቴክኖሎጂ ውርስ ማለቴ ነው፡፡ ነገር ግን ሙሉ በሙሉ ውርስ ይኖራል ብሎ መናገር ይከብዳል፡፡ የጎንደርን ኪነ-ህንፃዎች አንቺ ቅድም እንደገለፅሽው የውጭ ዜጎች ናቸው የገነቡት ይላሉ፤ እኔ በፍፁም በዚህ አልስማማም፡፡ የኪነ-ህንፃ ጥበብ ልክ እንደ ሙዚቃ የአለም ቋንቋ ነው፡፡ አንዲት አገር የራሷ ወጥ የሆነ የኪነ-ጥበብ ህንፃ የላትም፡፡ በምን ምክንያት ካልሽ … በእኛ በሰዎች ምክንያት፡፡ ሰው የተለያየ የህይወት ውህደት አለው፤ ይዘዋወራል፡፡ ሲዘዋወር አካባቢውን ይመስላል፤ ከአካባቢው የሚወስደውም ጥበብ ይኖራል፡፡
ያ ሰው ከሄደበት አካባቢ የወረሰውን ጥበብ፣ ሌላ ቀን የራሱ አድርጎ ይተረጉመዋል፤ ነገር ግን የነበረበት አካባቢ ተፅዕኖ ያርፍበታል፡፡ በዚህ የተነሳ ኪነ-ህንፃ የዓለም ቋንቋ ነው ይሉታል፡፡ እዚህ አካባቢ የፖርቹጋል፣ የህንድ፣ የአርመንና የሞሪሽየስ ዜጎች ነበሩ፡፡ በእርግጥ ከጎንደር በፊት የተሰሩ የአክሱም፣ የላሊበላና የየሀ ህንፃዎች አሉ፡፡ ሰዎች እስካሉ ድረስ እንኳን ጥበብ ዘርም ይቀያየራሉ፤ ከዚህ አንፃር የጎንደር ኪነ-ህንፃዎች የእነዚህ አገር ሰዎች ተፅዕኖዎች አለበት ይባላል፡፡
ከስድስቱ የፋሲል አብያተ መንግስታት አንዱ፣ በህንዳዊ የኪነ-ህንፃ ባለሙያ እንደተሰራ ይነገራል። እውነት ነው?
እርግጥ አብዱልከሪም የሚባል ህንዳዊ የኪነ-ህንፃ ባለሙያ በአፄ ፋሲለደስ ዘመን ነበር፡፡ እንደሚታወቀው አፄ ፋሲል አባታቸው አፄ ሱስንዮስ የካቶሊክን እምነት ለማስፋፋት ጥረት ያደርጉ ስለነበር በ1622 (ቅድመ ክርስቶስ ልደት) በርካታ ህዝብ አልቋል፡፡ አፄ ፋሲል ይህን አልተቀበሉም ነበር፡፡ የንግስና ዙፋኑን ሲይዙ 7 ሺህ ገደማ የካቶሊክ ሚሽነሪዎችን ከኢትዮጵያ አስወጥተዋል፡፡ የዛን ጊዜ ታዲያ ኢትዮጵያ ቢያንስ ለ200 ዓመት በሯን ለአውሮፓውያን  ዘግታ ነበር፤ ይህ “የጨለማ ዘመን” እያሉ የሚጠሩት ነው፡፡ ስለዚህ አብዱልከሪም የተባለው ህንዳዊ ሰውዬ ምንም እንኳ ሙስሊም ቢሆንም በኪነ-ህንፃ ጥበብ የተካነ ስለነበር፤ ከአባ ገ/እግዚያብሔር ጋር በመሆን የንጉስ አፄ ፋሲልን ቤተ መንግስት እንዲሰራ ተደርጓል፡፡ በዚህ ምክንያት የህንዶች ኪነ-ህንፃ ተፅዕኖ አለበት፡፡
እስቲ ወደ እርስዎ የአስጎብኚነት ጊዜ እንመለስ። ዝነኛ አስጎብኚ እንደነበሩና እንደነ ሲኤንኤን፣ ቢቢሲ እና መሰል ዓለም አቀፍ ሚዲያዎች ዘጋቢ ፊልም ለመስራት ሲመጡ፣ በሰከንድ 120 ዶላር ለእርሶ እየከፈሉ በሙያዎ ያገለግሏቸው እንደነበር ሰምቻለሁ፡፡ እውነት ነው? እስቲ ያጫውቱኝ…
ይህ እንግዲህ በፈረንጆቹ 1991 ዓ.ም አካባቢ ነው፡፡ ያኔ “ፍሮም ፖል ቱ ፖል” የተሰኘ ፊልም ተሰርቶ ነበር፡፡ የዛን ጊዜ አብሬ ሰርቻለሁ፤ ክፍያው በሰከንድ ሳይሆን በሰዓት ነበር፡፡ በሰዓት 150 ዶላር! ለእኛ አገር ትልቅ ይመስላል እንጂ ለእነሱ በጣም ዝቅተኛ ክፍያ ነው፡፡ እነዚህ ሰዎች ገና ከለንደን ከመነሳታቸው ከአንድ ወር በፊት ነው አፈላልገው ያገኙኝ፡፡ ከዚያም ያንን ፊልም ሰርተናል፡፡ ከቢቢሲ በኋላ ከሌሎችም የፊልም ቡድኖች ጋር ብዙ ስራዎችን ሰርተናል፡፡ ለምሳሌ ከጀርመንና ከጣሊያን፣ የፊልም ቡድኖች ጋር ሰርቻለሁ፡፡ ከፍተኛ የህይወት ልምድም አግኝቼበታለሁ፡፡
በጎንደር ከተማ የመንግስት ሰራተኛ ሆነው መኪና የነበረዎት ብቸኛው ሰው እንደነበሩም ሰምቻለሁ …
(ሳ…ቅ!) በአንዳንድ አጋጣሚ በግልሽ ቢዝነስ ስትሰሪ ገንዘብ ታገኛለሽ፡፡ ስለዚህ መኪና መግዛት ቻልኩ፡፡ የዛን ጊዜ መኪና እንደአሁኑ ውድ አልነበረም፤ እኔ በገዛሁበት ወቅት 50ሺ ነበር ዋጋው። የዛሬ 12 ዓመት አካባቢ ማለት ነው፡፡ እርግጥ ያኔ ብሩ በደንብ ዋጋ ነበረው፡፡ ስለዚህ በዚያን ወቅት መኪና መግዛት ያን ያህል የሚያስደንቅ ነገር አልነበረም፡፡
የበፊቷ መኪና ተቀየረች ወይስ…
አልተቀየረችም ራሷ ናት፤ አዲስ አበባ ነው አሁን ያለችው፡፡
ስለ አገራችን ቱሪዝም ስታስብ የሚቆጭህ ነገር ምንድን ነው?
አሁን የሚቆጨኝ ነገር የለም! እኔ ቱሪዝምን በአስተሳሰብ ደረጃ ተረድቼ ስሰራ በነበረበት ወቅት ብዙ ሰው ገና አልተረዳውም ነበር፡፡ ቱሪዝምን የምቾት፣ የቅንጦትና የመዝናናት አድርገው የሚያዩት ወገኖች ነበሩ፡፡ ቱሪዝም ግን እንደዛ አይደለም፡፡ ቱሪዝም የስራ እድል ፈጣሪ ነው፤ ዳቦ ነው፤ ሰላም ነው፤ ሁሉም ነገር ማለት ነው፡፡ አገርሽ ውስጥ ያለውን የባህልና የታሪክ ቦታዎች የምትሸጭበትና የስራ እድል የሚፈጥር ኢንዱስትሪም ነው፡፡ ከዚህ አንፃር ሲታይ የዚያን ጊዜ ሰዎች ቱሪዝምን የተረዱበት አስተሳሰብ ትክክል አልነበረም፡፡ እናም ሰው መቼ በትክክል እንደሚገባው፣ ገብቶትም መቼ ወደ ቢዝነስ እንደሚቀይረውና ተጠቃሚ የሚሆንበትን ቀን እናፍቅ ነበር፡፡ በአሁኑ ሰዓት ግን ሁሉም ሰው ስለቱሪዝም ያወራል፡፡ ስለ ገፅታ ግንባታው፣ ስለ ስራ ፈጣሪነቱና ስለተያያዥ ጉዳዮች ሰው ሲናገር ስሰማ በጣም እደሰታለሁ፤
ምክንያቱም ማንም ሳይረዳሽ ብቻሽን ስለቱሪዝም የምታወሪበት ጊዜ አልፎ አሁን አጋር ስታገኚና ሰው ሲገባው በጣም ያስደስትሻል፡፡
በወሬ ብቻ ነው ወይስ በተግባርም ነው?
አገሪቱ በዚህ ቅኝት ውስጥ እየገባች ነው ብሎ መናገር ይቻላል፡፡ ምክንያቱም ወደ ኢንዱስትሪው እንሸጋገራለን የሚል እቅድ ላይ ነው ያለነው፡፡ ወደ ኢንዱስትሪ ዘመን ሲገባ የበለጠ የሚያይለው የአገልግሎቱ ዘርፍ ነው፡፡ አሁን አገራችን ወደዚያ እየሄደች ነው፡፡ የቱሪስቱ ፍሰት እየጨመረ ነው። የበላይ አመራሮችና ውሳኔ ሰጪ አካላትም ስለቱሪዝም እያቀነቀኑ ነው፡፡ የትራንስፎርሜሽን ኤጀንሲ ተቋቁሟል፡፡ ከዚያ ባሻገር የአገሪቱን የቱሪዝም ምክር ቤት የሚመሩት ጠቅላይ ሚኒስትሩ ናቸው፡፡ ይህን ስታይ አገሪቱ ወደ ቅኝቱ ገብታለች ማለት እችላለሁ፡፡ እና ቁጭት የለኝም፤ እንዲያውም በጣም ደስታ ነኝ፡፡
ጎንደር ባሏት ታሪካዊ መስህቦች የሚገባትን ያህል ተጠቅማለች ይላሉ?
እዚህ ላይ ነው ወሬ የምናቆመው! ከተማዋ ያላትን ሀብት በአግባቡ አልምታ፣ የህብረተሰቡን ግንዛቤ አሁን ካለው የበለጠ አስፍታ፣ ህዝቡን ቀጥተኛ ተጠቃሚ አድርጋ የማስኬድ ስራ ገና ይቀራታል፡፡ ቱሪዝም ኢትዮጵያ ውስጥ የ30 እና የ40 ዓመት እድሜ ነው ያለው፡፡ ቅርስ አጠባበቅም እንደዚሁ! ምክንያቱም ቱሪዝም ካልሽ የምትሸጪው ቅርስ ስለሆነ፡፡ ኢትዮጵያ እኮ ከ80 በላይ ብሄር ብሄረሰቦች፣ ከ35ሺህ በላይ ገዳማትና ቤተክርስቲያናት፣ ከ25 በላይ ከፍታቸው ከ4ሺህ ሜ በላይ የሆኑ ተራሮች፣ በምስራቅ አፍሪካ ትልቁ የስምጥ ሸለቆ ስክራች መነሻና ሌሎች አገሮችን የሚያቋርጥ ስምጥ ሸለቆ እንዲሁም አሁንም በአይን የሚታይና አክቲቭ የሆነ እሳተ ጎመራ ያላት ናት። ይህም ሆኖ ቱሪዝም አሁንም በአገራችን ጨቅላ ነው፡፡ ይህንን ወደ ጥቅም ለመለወጥ እኔም፣ አንቺም ሌላውም በየሞያው የቤት ስራ አለበት፡፡ አለቀ፡፡
አሁን ቆመን የምንነጋገርበት ቦታ በእነ ፋሲለደስ ዘመን ራሶችና ተመሳሳይ ስልጣን የነበራቸው ሰዎች የሚኖሩበት “ራስ ግንብ” ነው፡፡ ዛሬ እዚህ ቦታ የተገናኘነውም የጎንደር እህት ከተማ በሆነችው የፈረንሳይ ቬንሰን ከተማ እድሳት ተደርጎለት የምርቃት ስነ-ስርዓቱ በመሆኑ ነው፡፡ በእድሳቱ የተነሳ “ራስ ግንብ” ብቻ ሳይሆን ሌሎችም አብያተ መንግስታት ምንነታቸውን እና የቀድሞ መስህብነታቸውን ያጣሉ የሚል ስጋት አለ፡፡ ይህ እንዳይሆን ምን ምን ቅድመ ጥንቃቄዎች ይደረጋሉ?
አሪፍ ጥያቄ ነው! አገራችን እንደምታውቂው የገንዘብ እጥረት አለባት፡፡ ይህንን ነገር ለመሸፈን ከተሞች አንዳንድ ሁነቶችን ማዘጋጀት አለባቸው፡፡ የገንዘብ ሁኔታ እንዲጎለብት የተለያዩ ፕሮጀክቶችን በመፍጠርና ስምምነቶችን በማድረግ፣ ከእነዚያ የአውሮፓ ከተሞች ተሞክሮዎችን ይወስዳሉ፤ በገንዘብም ይደጎማሉ፡፡ የጎንደር የቬንሰን ታሪክም ይሄ ነው፡፡
ይህን ፕሮጀክት የጀመሩት እርስዎ ነዎት ይባላል?   
ትክክል ነው! ፕሮጀክቱን የጀመርኩት እኔ ነኝ፡፡ ፕሮጀክቱን ቢያንስ ለስድስትና ለሰባት ወር ብቻዬን ነው የሰራሁት፤ ማንም ሰው አያውቅም ነበር፡፡ ከዚያ በኋላ ነው በግልፅ ወደ ከንቲባ ጽ/ቤትና ወደ ከተማ አስተዳደሩ ያሸጋገርነው፡፡ እነዚህ ሰዎች ጎንደር የቬንስን እህት ከተማ እንደመሆኗ፣ የእነሱም ከተማ ስለሆነች ይህን ራስ ግንብ ማደስ እንደሚፈልጉና የሙዚየም፣ የሀንድክራፍትና የቱሪዝም ልማነት እንዲሆን ገንዘቡን አቀረቡ፡፡ የግንቡ ፕሮጀክት አራት ምዕራፍ ነው ያለው፡፡
አንዱ ሙዚየም ልማት ነው፡፡ ሁለተኛው የሀንድክራፍት ልማት ሲሆን ሶስተኛው ቱሪዝም ልማት ነው፡፡ አራተኛው ደግሞ ግንቡን መጠገን ነው፡፡ አሁን የተሰራው የፕሮጀክቱ አራተኛ መዕራፍ ነው፡፡ የግንቡ ጥገና አልቆ ዛሬ ሊመረቅ እስፍራው ተገኝተናል፡፡
ይህ ግንብ ሲጠገን፣ የዩኔስኮ ንብረት የዓለም ህዝብ ንብረት በመሆኑ፣ ሶስት ነገሮች መጠበቅ አለባቸው፡፡
አንደኛው ኦተንትሲቲ (የዱሮ ይዞታውን የጠበቀ መሆን አለበት)፣ ይህ ማለት ለእድሳቱ የምንጠቀመው እንጨት፣ ድንጋይና ሌሎች ቁሳቁሶችም ጭምር የዱሮ መሆን አለባቸው ማለት ነው፡፡ ሁለተኛው ድሮ ከነበረው ከባቢ ጋር ቅንጅት (integrity) ያለው መሆን አለበት።
ከኢትዮጵያ ኪነ-ህንፃ ሁኔታ ጋር የተስማማና የተቀናጀ መሆን አለበት፡፡ በሶስተኛ ደረጃ “ሲንክሮናይዜሽን” የሚባል ነገር አለ፡፡ ይሄ ማለት አዲስ እንጨት ለእድሳቱ ካስገባሽ አዲስ ለመሆኑ ምልክት ማስቀመጥ አለብሽ፡፡ እነዚህ ሶስት መሰረታዊ ጥንቃቄዎች ተሟልተው ሲታደሱ ቅርሱ የቀደመ ምንነቱን አያጣም፡፡ ይህ ራስ ግንብም በዚህ መሰረት ነው የታደሰው፡፡
እርስዎ ሃገርዎን እንደሚያስጎበኙት ውጭ አገራትን የመጎብኘት ዕድል ገጥመዎታል? እስቲ ስለሌሎች አገራት አስጎብኚዎች ይንገሩኝ…
ለጉብኝት የሄድኩባቸው የውጭ አገሮች ብዙ ላይሆኑ ይችላሉ፤ ነገር ግን በሌላም ስራ የሄድኩባቸው ብዙ ቦታዎች አሉ፡፡ ከአፍሪካ ብንጀምር ሱዳን፣ ኬንያ፣ ዚምባብዌ… ወደ አውሮፓ ስንመጣ ትምህርቴን አልጨረስኩም እንጂ የመጀመሪያ ስኮላርሺፕ ያገኘሁት ቡልጋሪያ ነበር። ምስራቅ አውሮፓን ብትወስጂ ሀንጋሪ፣ ራሺያ እና ሌሎችንም አውቃለሁ፡፡ ከምዕራብ አውሮፓ ፈረንሳይን አይቻለሁ፡፡ ሁለት ጊዜ የመሄድ እድል ገጥሞኛል፡፡ ህንድ ሄጃለሁ፡፡
እንግሊዝም እንዲሁ። የማስጎብኘት ሁኔታው እንደየአገሩ ይለያያል፡፡ በሄድኩባቸው ቦታዎች ሁሉ ጉብኝት አድርጌያለሁ፤ ለቬንሰንም ጉዳይ ፈረንሳይ ሄጃለሁ፣ በአስጎብኚም ጎብኝቻለሁ፡፡ አስጎብኚ ለመሆን የታሪክ ሰው መሆን ያስፈልጋል ብለው ያምናሉ?
የታሪክ ሰው መሆን ያን ያህል ላያስፈልግ ይችላል፡፡ ቢሆንም ግን ጥሩ ነው፡፡ ዋናው ልብ ልንል የሚገባው አስጎብኚ ሁሉም ነገር ማለት ነው፡፡ ቀደም ሲል እንዳልኩት አስጎብኚ ምንም ነገር “አላውቅም” ማለት የለበትም፡፡
ፖለቲከኛ፣ የባዮሎጂ ሰው፣ የጂኦሎጂ ሰው፣ አርኪዎሎጂስት፣ የታሪክ ሰው፣ …ሁሉንም መሆን አለበት፡፡
ዘርፈ-ብዙ እውቀት ያስፈልገዋል፡፡