Administrator

Administrator

በቀድሞው የቢቢሲ ጋዜጠኛ ኪት ባወርስ ተጽፎ በሻማ ቡክስ የታተመው “Imperial Exile” የተሰኘ መፅሐፍ ትላንት ምሽት በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ፣ተፈሪ መኮንን አዳራሽተመረቀ፡፡ መጽሐፉ በእንግሊዝኛ ቋንቋ የተዘጋጀ ሲሆን ቀዳማዊ ኃይለስላሴ ከ1936-40በእንግሊዝ አገር ያሳለፉትን የስደት ህይወት እንዲሁም ወደ አገራቸው የተመለሱበትን ሁኔታያስቃኛል ተብሏል፡፡ በ260 ገፆች የተሰናዳው መጽሐፉ፤በ270 ብር ለገበያ ቀርቧል፡፡

Saturday, 28 May 2016 15:48

የነፃ ፕሬስ ጥግ

ሚዲያውን የሚቆጣጠር ሁሉ፣
አዕምሮንም ይቆጣጠራል፡፡
ጂም ሞሪሰን
- ሚዲያ እንደ ሌሎች ነገሮች ሁሉ
ሊገዛ ይችላል፡፡ ሁሉም ነገር የራሱ ዋጋ ያለው
ይመስላል፡፡ ነፃ ፕሬስም ጭምር፡፡
ላንስ ሞርካን
- ነፃ ፕሬስ ጥሩ ወይም መጥፎ ሊሆን
ይችላል፡፡ ነፃነት በሌለበት ግን ያለጥርጥር
መጥፎ ከመሆን ውጭ ሌላ ዕድል የለውም፡፡
አልበርት ካሙ
- በአገርህ ውስጥ ነፃ ፕሬስ ከሌለ
በቀር ጋዜጦችን መግዛትና ዜና መከታተል
አያስፈልግም፤ ምክንያቱም ውሸቶችን
ማዳመጥ አስፈላጊ አይደለም! አንድ ተጨባጭ
መረጃ እንደሆነ ታገኛለህ፡- በሚመሩህ ሰዎች
እየተታለልክ ነው! ይሄ ለአንተ በቂ መረጃ
ነው፡፡
ሜህሜት ሙራት አይልዳን
- ሁሉም ፀሐፊ የየራሱን ውሸቶች
ይናገር፡፡ ያ ነው የፕሬስ ነፃነት፡፡
ኖርማን ሜይለር
- በእኔ አስተያየት፣ የዲሞክራሲ
የማዕዘን ድንጋይ ነፃ ፕሬስ ነው፡፡
ሚሎስ ፎርማን
- ወደ ጋዜጠኝነት ሙያ የመጣነው
ታዋቂ ለመሆን አይደለም፡፡ እውነቱን
መፈለግን መልሶቹን እስክናገኝ ድረስ
በመሪዎቻችን ላይ የማያቋርጥ ጫና ማድረግ
ሥራችን ነው፡፡
ሔለን ቶማስ
- ጥሩ ጋዜጠኝነት፣ ጥሩ ቴሌቪዥን
ዓለማችንን የተሻለች የመኖሪያ ሥፍራ
ያደርጓታል ብዬ አምናለሁ፡፡
ክርስቲያኔ አማንፖር
- በጋዜጠኝነት የምታምን ከሆነ፣ ጥሩ
ጋዜጠኞችን አትሳደብም፡፡
ሲድኒ ስቻንበርግ
- ዓላማህ ዓለምን መለወጥ ከሆነ
ጋዜጠኝነት በጣም ፈጣኑ የአጭር ጊዜ መሳሪያ
ነው ብዬ አሁንም ድረስ አምናለሁ፡፡
ቶም ስቶፓርድ

ከ 300 ሺ በ ላይ ሶማሊያውያን ስ ደተኞችን ወደ አገራቸው ለመመለስ ወ ስናለች
          ኬንያ በአለማችን በትልቅነቱ ቀዳሚውን ስፍራ የሚይዘውን የዳዳብ የስደተኞች መጠለያ ጣቢያ ለመዝጋት መወሰኗን የአገሪቱ ምክትል ፕሬዚዳንት ዊሊያም ሩቶ መግለጻቸውን ተከትሎ፣ የተባበሩት መንግስታት ድርጅት ውሳኔውን እንደሚቃወመው ማስታወቁን ኦል አፍሪካን ዶት ኮም ዘገበ፡፡
የተመድ ዋና ጸሃፊ ባንኪ ሙን፤ ኬንያ ግዙፉን የስደተኞች መጠለያ ጣቢያ ለመዝጋት መወሰኗ፣ በመጠለያ ጣቢያው ውስጥ የሚገኙ በመቶ ሺዎች የሚቆጠሩ ስደተኞችን ለከፋ አደጋና ጥፋት የሚዳርግ በመሆኑ ውሳኔውን እንደሚቃወሙት ማስታወቃቸውን ዘገባው ጠቁሟል፡፡ የኬንያ ምክትል ፕሬዚዳንት ዊሊያም ሩቶ ባለፈው ሰኞ በቱርክ መዲና ኢስታምቡል በተካሄደው የዓለማችን የሰብዓዊ ጉዳዮች ጉባኤ ላይ የአገሪቱ መንግስት የስደተኞች መጠለያ ጣቢያውን በመዝጋት 300 ሺህ ያህል ሶማሊያውያን ስደተኞችን ወደመጡበት ለመመለስ ያሳለፈው ውሳኔ የማይቀለበስ ነው ሲሉ መናገራቸውን ያስታወሰው ዘገባው፣ አለማቀፉ ማህበረሰብ ስደተኞቹን መልሶ ለማስፈር ተገቢውን ድጋፍ እንዲያደርግ ጥሪ ማቅረባቸውንም አመልክቷል፡፡ የኬንያ መንግስት የስደተኞች መጠለያ ጣቢያዎችን በአንድ አመት ጊዜ ውስጥ ሙሉ ለሙሉ ለመዝጋት የወሰነው፣ የሽብርተኞች መደበቂያና ለአገሪቱ ደህንነት ስጋት በመሆናቸውና ለአካባቢው አደጋ ስለሆኑ ነው ማለቱን የጠቆመው ዘገባው፣ተመድ ውሳኔውን ተቃውሞታል፡፡

     በግል ህይወትም ይሁን በድርጅታዊ አሰራርና ዕድገት ውስጥ መሆን ያለበትና እየሆነ ያለው ለየቅል ሊሆን ይችላል፡፡ ይህ ክስተት ደግሞ ብዙ ግዜ የሚያጋጥም ጉዳይ ነው፡፡ በርካታ ባለድርሻ አካላት ባሉባቸው ሰፊ ሃገራዊ ጉዳዮች ላይ ክፍተቱ ገዝፎ እንመለከታለን፡፡ እንደ ግለሰብ አንድ ሰው፣በህይወቱ ውስጥ መሆን ባለበትና እየሆነ ባለው ኩነት መካከል ሰፊ ልዩነት ሲኖረው፣ ወደ መፍትሔ የሚወስደው ተጨባጭ ርምጃ፣መጀመሪያ አሁን ያለበትን ሁኔታ በደንብ መረዳት፣ ቀጥሎም ምን መሆን እንዳለበት በግልፅ በማስቀመጥ ወደዛ የሚያደርሱትን መንገዶችና ስራዎች ብሎም በአጠገቡ ያሉ ሊያግዙት የሚችሉ አካላትን መለየት ይሆናል፡፡ አብዛኛው ሰው በየትኛውም አለም ይኑር ተመሳሳይ ሂደት ሲከተልም እናያለን፡፡ ይህ የለውጥ ሂደት ከግለሰብ ጀምሮ ለድርጅት፣ ለአገር ብሎም ለአለም የሚሰራ ነው፡፡ ለውጥ ለማምጣት ሙሉ ሂደቱን መጓዝ አለብን ፤ ግማሽ መንገድ ተጉዞ ሙሉ ውጤት ማምጣት አይቻልምና፡፡ ችግሩ በበርካታ ሃገራዊ ጉዳዮች ዙሪያ የሚደረጉ ውይይቶች በአብዛኛዉ ባሉ ሁኔታዎች ላይ ብቻ በማተኮር መሆን ያለበትን ማስቀመጥ አለመቻላቸዉ ነዉ፡፡ ስለሆነም ቀጣዩና የሚፈለገዉ ሂደት መምጣት አለበት ፤ ውይይቶች ወደ ላቀ ደረጃ መሸጋገር አለባቸው፡፡ለምሳሌ ባለን የመገናኛ ብዙሀን ደስተኛ ካልሆንን ምን አይነት የመገናኛ ብዙሀን እንፈልጋለን? ያን የምንጓጓለትን የመገናኛ ብዙሃን ዕዉን ለማድረግስ ምን መስራት ይጠበቅብናል ብለን መጠየቅ ያስፈልጋል፡፡ በተመሳሳይ በአገራችን ያለው የበጎ አድራጎት ድርጅቶችና ማህበራት ዘርፍም የዚህ የውይይቶች ግማሽ መንገድ ላይ መቆም ችግር ማሳያ ነው፡፡ ከፍተኛ የመንግስት ባለስልጣናት፣ ደጋፊ አካላት፣ የመገናኛ ብዙሀን፣ ምሁራን፣ የንግዱ ማህበረሰብ
ብሎም መላው ህብረተሰብ፣ በአገራችን ባለው የበጎ አድራጎት ድርጅቶችና ማህበራት ዘርፍ (ሲቪክ
ማህበራት) ደስተኛ እንዳልሆኑ ይገልፃሉ፡፡ የበጎ አድራጎት ድርጅት አሰራር ከፅንሰ ሀሳቡ አንፃር መሆን ያለበትና እየሆነ ያለው ይለያያል የሚል አስተያየት ከብዙ አቅጣጫ ይደመጣል፡፡ በበጎ አድራጎት ድርጅቶችና ማህበራት በኩል ደግሞ መንግስትና የመገናኛ ብዙሀን ለስራችን ተገቢውን እውቅና አይሰጡም በማለት ይወቅሳሉ፡፡ እነዚህ አስተያየቶች ከፊል እውነታ ሊኖራቸው ይችላል፡፡ ዋናው እውነታ ግን ውይይቱ ግማሽ ሂደት ላይ መቆሙ ነው፡፡ ይህ ማለት ከላይ የተዘረዘሩት ሁሉም አካላት በአገራችን ባለው የበጎ አድራጎት ድርጅቶችና ማህበራት ደስተኛ ካልሆኑ ቀጥሎ መምጣት ያለበት እና መሆን ያለበት ምንድነው? ምን አይነት የበጎ አድራጎት ድርጀቶችና ማህበራት ዘርፍ መፍጠር እንፈልጋለን? ምን መደረግስ አለበት? ከማን ምን ይጠበቃል? ወደሚል ሰፊ የውይይትና የመፍትሔ ደረጃ ማደግ ይኖርበታል፡፡ የአመለካከት ችግሩ የሚጀምረው የዘርፉን ሚና አሳንሶ ከማየት ነው፡፡ ይህ ክፍተት ሚናቸውን ከሚያመጡት ገንዘብ መጠን ጋር በዋናነት በሚያያይዙት የበጎ አድርጎት ድርጅቶችና ማህበራት ይጀምራል፡፡ መንግስት በበኩሉ ደግሞ ከዕለት ምጽዋት ጋር በሚመሳሰል መልኩ በጎ የማድረግ ስራ ብቻ አላቸው ብሎ ያስባል፡፡ ይህ የመንግስት አመለካከትም የበጎ አድራጎት ድርጅቶችና ማህበራት
ወሳኝ የልማት አጋር ናቸዉ ከሚለዉ ብሂል ጋር ይጋጫል፡፡ ይህ ፅሁፍም እየሆነ ባለው ላይ ያተኮረ
ስላልሆነ ወደ ቀጣይና  የተሻለ ደረጃ እንዴት እንሸጋገር የሚለዉ ላይ ገንቢ ትንተና ያደርጋል፡፡
በእርግጥ ይህ ፅሁፍ ምን መሆን እንዳለበት በቀጥታ የማስቀመጥ አላማም ሆነ አቅም የለውም፡፡
የዚህ ፅሁፍ አላማ ውይይቶችን ማሻሻል ነው፤እየሆነ ባለው ላይ ከመወቃቀሰ ይልቅ መሆን
ወዳለበት እንድንመለከት ጥያቄውን ማንሳት ነው፡፡
መንግስት ምን አይነት የበጎ አድራጎት ድርጅቶችና ማህበራት ዘርፍ ነው መፍጠር የሚፈልገዉ?
ሁላችንንም የሚያስደስተንና እንደ አገር የምንኮራበት ዘርፍ ለመፍጠር መንግስት ምን ለማድረግ
አቅዷል? እንደመፍትሄ ሃሳብም ዘርፍ መሻሻልና ማደግ ካለበት መሪ ይፈልጋል፤ስለዚህ መንግስት
ሴክተሩን የመምራትና የማገዝ ሃገራዊ ግዴታ አለበት፡፡ ይህ ማለት የዘርፉ ነፃነት እንደተጠበቀ ሆኖ፣
መንግስት የመንግስት ሚናውን በመወጣት ለዘርፉ የተሻለ የስራ ማዕቀፍ በመፍጠር ረገድ ከፍተኛ
ድጋፍ ማድረግ አለበት ማለት ነው፡፡
የበጎ አድራጎት ድርጅቶችና ማህበራት ሀላፊዎች በበኩላቸዉ፤በጎ የማድረግ ፅንሰ ሀሳብንና አሁን
በተግባር እየሆነ ያለውን ማነጻጸርና ራስን መገምገም፣ ከዚህ አልፎም መሆን ወዳለበት አቅጣጫ
መምጣት ይኖርባቸዋል፡፡ ማህበረሰባችን አሉታዊም ሆነ አዎንታዊ ዕይታዎችን
የሚያንጻባርቀዉ፣ከሚያየዉና ከሚሰማዉ በመነሳት ነዉ፡፡ ስለሆነም አሉታዊ አመለካከት ቢኖር
ሁልጊዜ ስህተት ነዉ ለማለት ያስቸግራል፡፡ የበጎ አድራጎት ድርጅት ውስጥ መስራት ማለት ጥሩ
ደሞዝ ከማግኘት የዘለለ ትርጉም እንዳለው በአሰራራቸንና አኗኗራችን ማሳየት አለብን፡፡ ዋናው
ጉዳይ የሚኮረኩረን ፣የማያስተኛንና የተነሳንበት ዓላማ ህዝብን የመደገፍና የመርዳት ብሎም
የመንግስትና የህዝብ ወሳኝ የልማት አጋር መሆናችንን ማስረገጥ ላይ ነዉ፡፡ የበጎ አድራጎት ድርጅት ሀላፊ፤በህብረተሰቡ በበጎ ስራው እና ተግባሩ የሚከበር መሆን ያለበት ሲሆን አሁን ያለው አመለካከት ግን ሙሉ በሙሉ ከዚህ ጋር አብሮ ይሄዳል ለማለት ያስቸግራል፡፡ ይህ ማለት ግን ማህበረሰባችን በሙሉ ተመሳሳይና ለሴክተሩ የተዛባ አመለካከት አለዉ ማለት አይደለም፡፡ መልካም የሚሰሩ እጅግ በርካታ ቁጥር ያላቸዉ የበጎ አድራጎት ድርጅቶችና ማህበራት እንዳሉ ሁሉ፣ በአግባቡ የማይሰሩ የሴክተሩን ስም ጥላሸት የሚቀቡ በጣም ጥቂት ድርጅቶች እንዳሉም ይታመናል፡፡ይህን ጉዳይ ከስር መሰረቱ ስንመረምረው፣ማየት ያለብን በአገራችን መፍጠር የምንፈልገውን ዘርፍ አሁን ካለበት ደረጃ ጋር በማነፃፀርና የህዝባችንን አኗኗር፣ ባህልና ወግ ግምት ዉስጥ በማስገባት እንጂ በቀጥታ ከሌላ አገር ጋር በማነፃፀር መሆን የለበትም የሚል ዕምነት አለን፡፡ ይህ ማለት ግን ጠቃሚ ተሞክሮዎች ከዉጭ አይወሰዱም ማለት አይደለም፡፡ በማንኛዉም ሰአትና
ጊዜ አገራችንን እና ህዝባችንን የበለጠ ተጠቃሚ ሊያደርግ የሚችል የአሰራር ስርአት ቢኖር ልምድ
መወሰዱ በበጎ ጎን የሚታይ ነዉ፡፡  የበጎ አድራጎት ድርጅቶችና ማህበራት ከተለመደው የበጎ አድራጎት ስራ በዘለለ በአገራችን ሁለንተናዊ ዕድገት ውስጥ ብዙ ሚና መጫወት ይችላሉ፤አለባቸውም፡፡ የሙያ ማህበራት የአንድን ሙያ ጥራት ከመጠበቅ እና ከማሳደግ አንፃር ትልቅ ስራ መስራት ይችላሉ፡፡ የተለያዩ አገር አቀፍ ህጎችና ፖሊሲዎች ሲወጡ ከሙያቸው ጋር በተያያዙ ጉዳዮች ዙርያ ጠቀሚ ግብአቶች መስጠት ይችላሉ፡፡ የተለያዩ ሀገራዊ እና ህዝባዊ የለውጥ ንቅናቄዎች ለማምጣት ሰንፈልግ የብዙሀን ማህበራት ንቅናቄውን መምራትና ማቀጣጠል ይችላሉ፤ ሌላም ሌላም፡፡  መንግስት አንድን አገር ሲመራ ሁሉንም ዘርፍ በእኩል መምራት ይጠበቅበታል፡፡ ይሄም በወሳኝ መልኩ ተቀራርቦ መስራትን ይጠይቃል፡፡ በዋናነት የአሰራር አቅጣጫ ከሚያስቀምጠው ከፍተኛው አመራር ማለትም፤ ከጠቅላይ ሚኒስትራችን ምን አይነት የበጎ አድራጎት ድርጅቶችና ማህበራት መፍጠር እንደሚፈልጉና ምን ምን እንዳቀዱ ማወቅ እንሻለን፤ይህ የሚሆንበት አሰራር መፈጠር አለበት፡፡ ከሙያ ማህበራት ጋር በተያያዘ የተለያዩ የሙያ ማህበራት እንዳሉ በራሱ ግንዛቤ የለም፡፡ ለምሳሌ
የጋዜጠኞች ማህበር፣ የሙዚቀኞች ማህበር፣ የሰአሊያንና ቀራፅያን ፣ የፊልም ሰሪዎች፣ የደራስያን
ወዘተ እያለ ይቀጥላል፡፡ ዘርፉ ይህን ሁሉ ይዞ ነው ሚናውን አሳንሰን እያየን ያለነው፡፡ ለእነኚህ
አካለትም የተመቻቸ የአሰራር ስርአት መፍጠር፤ ስራዎቻቸዉን ማየትና መገምገም፣ ለአሰራር
የማያመቹ ሁኔታዎችን በጋራ መለየትና መፍትሄ ማበጀት ሌላዉ የመንግስት ወሳኝ የስራ ሃላፊነት
ነዉ ተብሎ ይታመናል፡፡ ከዚህ ባለፈ በአገራችን የሚገኙ ደጋፊ አካላትም አሁን ባለው ዘርፍ ብዙም ደስተኛ አለመሆናቸውን ሲገልፁ ይደመጣል፡፡ በሌላ በኩል ደግሞ በበጎ አድራጎት ድርጅቶችና ማህበራት በኩል የደጋፊ አካላት የአሰራር ስርአቶች በተለይም ለሃገር በቀል ድርጅቶች የማያመቹና ይልቁንም ዉስብስብ መሆናቸዉ ይገለጻል፡፡ ይህም “እንዳያማህ ጥራዉ፣እንዳይበላ ግፋዉ” የሚለዉን የአባቶች ብሂል ያስታዉሰናል፡፡ ስለሆነም
ደጋፊ አካላት የሚያደርጉት እገዛ፣ የተሻለ ለውጥ ማምጣት እንዲችል ከታመነ በተለይም አገር በቀል
ድርጅቶች ያላቸዉን ስትራቴጂካዊ ጠቀሜታ ግምት ዉስጥ በማስገባት ለህዝብ እጅግ የቀረቡ
በመሆናቸዉ ይህንኑ መጠቀም መቻል ብልህነት ነዉ፡፡ የበጎ አድራጎት ድርጅቶችና ማህበራት:
መንግስትና የንግዱ ማህበረሰብ በጋራ የምንጋራው ዓላማና ራዕይ ይዘን ነገር ግን የተለያየ ሀላፊነት
ያለብን ባለ ድርሻ አካላት እንጂ ለብቻችን ተነጥለን የምንሰራው ስራ እንደሌለ በመገንዘብ፣ ተቀራርቦ ወደ መስራት በመምጣት ጠንካራ ዘርፍ መፍጠር እንደምንችል እናምናለን፡፡ የበጎ አድራጊነት ፅንሰ ሀሳብና አሁን የምንንቀሳቀስበትን ማዕቀፍ በመፈተሸ፣ ከፅንስ ሀሳቡ ጋር የሚሄድ አሰራርና እንቅስቃሴ መፍጠር መቻል አለብን፡፡ እነዚህንና በተጨማሪም እናንተ አንባብያን ባለድርሻ አካላት ምትጨምሩዋቸው ሀሳቦችን አንድላይ በማምጣት አሁን ካለን ደካማ የሆነ የበጎ አድራጎት ድርጅቶችና ማህበራት ዘርፍ ወደምንፈልገው እና መሆን ወዳለበት መውሰድ እንደምንችል ጠንካራ እምነት አለን፡፡ ይሄም የሚጀምረው ጉዳዩን ወደ ጋራ ውይይት በማምጣት ሲሆን ፤ ሂደቱን  ሀ ብለን ይሄው ዛሬ በዚህ ፅሁፍ ጀምረነዋል፡፡











Saturday, 28 May 2016 15:27

ቬንዝዌላ - የቅዠት አገር

አገሪቱ ለሃብታሙም ለድሃውም ሲኦል ሆናለች፡፡ የፋብሪካ ባለቤት መሆን፣ እዳ ነው፡፡ ትንሽዬ ምግብ ቤት ከፍቶ መስራት እንኳ፤ ትዕግስትን ያስጨርሳል፡፡ በየአመቱ ሰላሳ አይነት የስራ ፈቃዶችን ለማሳደስ መንከራተት የግድ ነው፡፡
ለአንድ ምናብ ቤት ወይም ለአንድ ፋብሪካ ሰላሳ የፈቃድ እድሳት! እንኳን ሰላሳ፣ አንዱን የስራ ፈቃድ ብቻ ማሳደስም መከራ ነው፡፡ ቢቢሲ ያነጋገረው የፋብሪካ ባለቤት፣ በየእለቱ ከሚያጋጥሙት መዓት መከራዎች መካከል፣ ቀላል የሚመስል አንድ ችግር ብቻ በመጥቀስ አስረድቷል፡፡ የመንግስት የቁጥጥር ብዛት አይጣል ነው፡፡
ፋብሪካው በየወሩ ለሰራተኞች “ሶፍት” መስጠት አለበት በሚል የሚደረግ፣ ቁጥጥር ብቻ፣ መከራውን አይቷል፡፡ “ሶፍት” እንደማንኛውም ሸቀጥ፤ በመንግስት ሱቆች ነው የሚቀርበው፡፡ ባለፋብሪካው፣ ቀኑን ሙሉ ወረፋ ይዞ፣ ሁለት ሦስት ሶፍት መግዛት ይችላል - እድለኛ ከሆነ፡፡ ብዙ ጊዜ አይገባኝማ፡፡ ወዲያው ያልቃል፡፡ ሌላኛው አማራጭ፣ በኮንትሮባንድ የገባ ሶፍት መግዛት ነው፡፡ ነገር ግን የኮንትሮባንድ “ሶፍት” መግዛቱ ከታወቀ፤ ከመከራ አያመልጥም - ፋብሪካው ይወረስበታል፡፡ ለሰራተኞች ሶፍት ካላቀረበም፣ ፋብሪካው በመንግስት ይወረሳል፡፡
ማምለጫ የለውም፡፡ ሶፍት እስኪገኝ ድረስ የፋብሪካውን ስራ ለማስቆም ሲገደድ አስቡት፡፡
ግን ይህንንም ማድረግ አይችልም፡፡ ስራ ያቆመ ፋብሪካ በመንግስት ይወረሳል የሚል ህግ ታውጇል፡፡
ቢቢሲ እንደዘገባው፣ የቬንዝዌላ መንግስት ሶሻሊዝምን አስፋፋለሁ በማለት፣ ከአንድ ሺ በላይ ፋብሪካዎችን ወርሷል፡፡ ፋብሪካዎቹን ምርታማ አደርጋለሁ ብሎ ነው የወረሳቸው፡፡ ግን አልቻለም፡፡ አብዛኞቹ የመንግስት ፋብሪካዎች እየሰሩ አይደለም ብሏል - የቢቢሲው ጋዜጠኛ፡፡
የምርትና የሸቀጦች እጥረት እንዲህ እየተባባሰ፣ አገሪቱ ዛሬ ገደል አፋፍ ላይ ደርሳለች፡፡
ነዋሪዎችን በማነጋገር ከቬንዝዌላ ዘገባ ያቀረበችው የሲኤንኤን ጋዜጠኛ፣ የሚላስ የሚቀመስ ምግብ እየጠፋ ነው ብላለች፡፡ በዋጋ ቁጥጥር ሳቢያ፣ ሸቀጦች ሁሉ ከገበያ ጠፍተዋል፡፡
እናም የአገሬው ሰዎች፣ ዘይትና ዱቄት፣ ጨውና ስኳር፣ ቲማቲምና ሳሙና ለመግዛት ከመንግስት ሱቆች ደጃፍ ከንጋት እስከ ምሽት ይሰለፋሉ፡፡ የሱቁ ደጃፍ ላይ የተጀመረው ወረፋ፣ ጥጋጥጉን እስከ ማዶ ሄዶ፣ መስቀለኛው መንገድ ላይ ወደ ግራ ታጥፎ፣ ሩቅ ጫፍ ድረስ ይቀጥላል፡፡
ከአምስት ሰዓት በኋላ ወረፋ የደረሰው ጐልማሳ፣ ዱቄትና ወተት አላገኘም፡፡ ቢጨንቀው፣ ሁለት ሊትር ክሬም ገዝቶ ወጣ፡፡
 ሌላ ነገር የለም፡፡ ከሦስት ቀን በኋላ ተመልሶ እድሉን ይሞክራል፡፡ በየቀኑ መሄድ አይቻልም፡፡ በሳምንት ሁለት ቀን ብቻ ነው የሚቻለው፡፡ የአንዱ ቤተሰብ ተራ፣ ሰኞና ሃሙስ ሊሆን ይችላል፡፡
የሌላኛው ቤተሰብ ደግሞ ማክሰኞና አርብ፡፡ አንዳንድ የባሰበት እድለ ቢስ፣ ዛሬ የወዛደሮች በዓል ዋዜማ ነው ተብሎ ቀኑ ያልፍበታል፡፡ሆስፒታሎችና ፋርማሲዎችም እንዲሁ፣ የመድሃኒት መደርደሪያቸው ኦና ሆኗል፡፡ ስካይ ኒውስ ረቡዕ እለት ባቀረበው ልዩ ዘገባ፣ የዋና ከተማዋን ሆስፒታሎች አሳይቷል፡፡
የምርመራ መሳሪያዎች አይሰሩም - በየኮሪደሩ ተወዝፈዋል፡፡ የምርመራና የታማሚዎች ክፍሎች፣ ኮሪደሮችና መፀዳጃ ቤቶች ቆሽሸው ይዘገንናሉ፡፡ ውሃ የለም፡፡
የህመም ማስታገሻና አሞክሳስሊን የመሳሰሉ ተራ መድሃኒቶች እንኳ ብርቅ ሆነዋል (ከውጭ አገር ፓናዶልና አሞክሳስሊን ገዝቶ የሚልክ ወዳጅ ዘመድ ካልተገኘ በቀር) የ21ኛው ክፍለ ዘመን የሶሻሊዝም አብዮተኛ ነኝ የሚል መንግስት፣ ቬንዝዌላን የቅዠት አገር አድርጓታል፡፡
 አሳዛኙ ነገር፣ እንዲህ አይነት መንግስት በምርጫ አሸንፎ ስልጣን መያዙ ነው፡፡   


እስካሁን በአምስት አመታት ውስጥ 800 ሚሊዮን በላይ አይፎኖችን በመሸጥ፣ 500 ትሪሊዮን ዶላር ገቢ አድርጓል - ግማሽ ትሪሊዮን መሆኑ ነው። በተመሳሳይ ጊዜ፣ ከአይፎን ተለቅ ያለ፣
ከላፕቶፕ አነስ ያለ፣ አዲስ ምርት ለገበያ አብቅቷል - አይፓድ። በ300 ሚሊዮን የአይፓድ ሽያጭ፣ 140 ቢሊዮን ዶላር አስገብቷል።

   ከመስከረም ወዲህ፣ በስድስት ወራት ውስጥ፣ እኛ ቀን ስንቆጥር፣ አፕል ኩባንያ የትርፋማነት ሪከርድ ለመስበር ከራሱ ጋር ሲፎካከር ከርሟል፡፡ ከ125 ሚሊዮን አይፎኖች ሽያጭ፣ ወደ ከሰማኒያ ቢሊዮን ዶላር በላይ ገቢ አግኝቷል - በግማሽ ዓመት፡፡ አይፓድ እና ኮምፒዩተሮችን ጨምሮ የ126 ቢሊዮን ዶላር ምርቶችን የሸጠው አፕል ኩባንያ፣ 29 ቢሊዮን ዶላር የተጣራ ትርፍ በማስመዝገብ ዓመቱን አጋምሷል።
በመጪው መስከረም አይፎን7 የተሰኘ አዲስ ሞባይል ለገበያ እንደሚያቀርብ የገለፀው አፕል፣ ከወዲሁ ከ70 ሚሊዮን በላይ ቀፎዎችን በጊዜ ለማድረስ ተፍተፍ እያለ ነው። ለምን? አሰፍስፈው የሚጠብቁ ብዙ ደንበኞች አሉት። አዲስ አይፎን ለገበያ በቀረበበት እለት፣ እጃቸው ውስጥ እንዲገባ ይፈልጋሉ። ባለፈው ዓመት እንደታየው፣ በመጀመሪያዋ እለት፣ እስከ አስር ሚሊዮን የሚደርሱ ደንበኞችን፣ በኢንተርኔት ማስተናገድና መሸጥ ይጠበቅበታል፡፡ የአፕል ታሪክ የተቀየረው የዛሬ 15 ዓመት ነው። ያኔ፣ የኮምፒዩተር ምርት ነበር፣ ዋነኛ የገቢ ምንጩ። ነገር ግን፣ ኮምፒዩተር በርካሽ  ሰርተው ለገበያ የሚያቀርቡ ብርቱ ተፎካካሪዎች መጡበት። ለኪሳራ ተጋለጠ። በእርግጥ ኪሳራው አልተደጋገመበትም። ከአንድ አመት ኪሳራ በኋላ፣ ማገገም ችሏል። ማገገም ብቻ ሳይሆን ትርፋማነቱ እጥፍ ድርብ ተተኮሰ፡፡ ምን አዲስ ነገር ተፈጠረ?
በ1995 ዓ.ም፣ አፕል የ6 ቢሊዮን ኮምፒዩተሮችን በመሸጥ፣ 70 ሚሊዮን ዶላር ትርፍ ነበር ያገኘው። ከአመት በኋላ ደግሞ፣ ትርፉ በሦስት እጥፍ ጨመረ፣ ሩብ ቢሊዮን ዶላር አተረፈ፡፡ በዚህ አላቆመም፡፡ በቀጣዩ አመት፤ እንደገና ትርፋማነቱ በአራት እጥፍ አደገ - ወደ 1.3 ቢሊዮን ዶላር። ከዚያም 2 ቢሊዮን ዶላር አተረፈ - የዛሬ አስር ዓመት በ1998 ዓ.ም።
ምን ተፈጠረ? አይፖድ  (IPOD) ተፈጠረ።
አፕል፣ ከኮምፒዩተር በተጨማሪ፣ የሙዚቃ ማከማቻና ማዳመጫ አይፖድ በማምረት ለገበያ ማቅረብ የጀመረው በ95 ዓ.ም ነው። በመጀመሪያው አመት አንድ ሚሊዮን አይፖዶችን በመሸጥ ተወዳጅነትን በማትረፉ፣ በሁለተኛው አመት ከሃያ ሚሊዮን በላይ አይፖዶችን፣፣ በሦስተኛው አመት 40 ሚሊዮን አይፖዶችን ቸብችቧል። ከዚያም ለተከታታይ አራት አመታት፣ ከሃምሳ ሚሊዮን በላይ አይፖዶችን፡፡
ታዲያ፣ ሁሉም ነገር አልጋ ባልጋ ሆኖለል ማለት አይደለም፡፡ ከጊዜ በኋላ፣ የአይፖድ ገበያው ቀንሶበታል። የአመት ሽያጩ፣ ወደ አርባ ሚሊዮን፣ ከዚያም ወደ ሰላሳ፣ ወደ ሃያ፣ ወደ አስር ሚሊዮን እየወረደ፣ ዘንድሮ ጨርሶ ተመናምኗል።
ደግነቱ፤ ያኔ የአይፖድ ገበያው ገና መቀዛቀዝ ሳይጀምር፣ አፕል ሌላ  ተአምረኛ ምርት ፈጥሯል - አይፎንን - በ1999 ዓ.ም።
በ2000 ዓ.ም አስር ሚሊዮን ገደማ አይፎኖችን ነበር የሸጠው። ከዚያማ፤ የአፕል ትልቁ የገቢ ምንጭ አይፎን ሆነ። ከአመት በኋላ ደግሞ፣ ሃያ ሚሊዮን አይፎኖችን። ዛሬ በአመት፣ አስር እጥፍ አይፎኖችን እየሸጠ ነው - ከሁለት ሚሊዮን በላይ።
እስካሁን፣ በአምስት አመታት ውስጥ ብቻ 800 ሚሊዮን በላይ አይፎኖችን በመሸጥ፣ 500 ትሪሊዮን ዶላር ገቢ አድርጓል - ግማሽ ትሪሊዮን መሆኑ ነው። በተመሳሳይ ጊዜ፣ ከአይፎን ተለቅ ያለ፣ ከላፕቶፕ አነስ ያለ፣ አዲስ ምርት ለገበያ አብቅቷል - አይፓድ (IPAD)። በ300 ሚሊዮን የአይፓድ ሽያጭ፣ 140 ቢሊዮን ዶላር አስገብቷል። ከአይፎን በመቀጠል፣ አይፓድ ሁነኛ የገቢ ምንጭ ሆነ ማለት ነው።
ግን እስከ መቼ? እስካሁን፣ በሁሉም መስክ ተዋጥቶለታል። የሞባይልን ገበያ የሚቀይር፣ በቴክኖሎጂ የረቀቀ አዲስ ምርት በማቅረብ፣ ከዚያም በየጊዜው በምርምርና በቴክኖሎጂ ምርቱን እያሻሻለ፣ በተወዳጅነት እዚህ ደርሷል። ግን እንደ ቀድሞው፣ በየአመቱ በአይፎን ሽያጭ ሪከርድ እየሰበረ መቀጠል አይችልም።
በአንድ በኩል፣ ከብርቱ ተፎካካሪው ከሳምሰንግ በተጨማሪ፣ እንደ ዚያውሚ የመሳሰሉ፣ በአነስተኛ ዋጋ፣ መካከለኛ ስማርት ፎኖችን የሚያቀርቡ ኩባንያዎች በርክተዋል።
በሌላ በኩል ደግሞ፣ ሞባይል ስልክ፣ እንደ ልብስ አይደለም - ሦስት አራት አይፎኖችን እያቀያየሩ መጠቀም ‘ኖርማል’ አይደለም። አንድ አይፎን በቂ ነው፡፡ ምናልባት በአመት በሁለት አመት አዲስ አይፎን ይቀይራል። አይፓድም እንደዚያው። ስለዚህ፣ የአይፎንና የአይፓድ ገበያ፣ በአጭር ጊዜ ውስጥ፣ እንደ አይፖድ ባይመናመንም፣ ያን ያህልም ይስፋፋል ተብሎ አይጠበቀም።
እና አፕል ምን አስቧል?
ያው፣ የአይፎንና የአይፓድ ምርቶቹን፣ እያሻሻለ መቀጠሉ አይቀሬ ነው። ነገር ግን፣ አዳዲስ ነገሮችንም ከፍቷል። እንደ ጉጉል፣ አፕልም፣ ‘ያለ ሾፌር የሚንቀሳቀሱ መኪኖችን’ ለመፈብረክ አዲስ ኢንቨስትመንት ጀምሯል።  የራሱ የመኪና ፋብሪካ አደራጅቶ፣ ሁለት ዓመት ባልሞላ ጊዜ ውስጥ፣ “ከሾፌር የፀዱ” መኪኖችን እያመረተ እንደሚሸጥ ገልጿል።
ከሰሞኑ ደግሞ፣ የኡበር አይነት፣ ዘመናዊ የታክሲ ስራ ጀምሯል - አፕል፡፡ ታዲያ ታክሲዎችን አያሰማራም፡፡ ማንኛውም ባለመኪና፣ በተመቸው ጊዜ የታክሲ አገልግሎት እንዲሰጥ፣ ከተሳፋሪ ጋር በኢንተርኔት ማገናኘት ነው ስራው። ቀላል ስራ እንዳይመስላችሁ። ኡበር፣ ዛሬ እጅግ ትልቅ ኩባንያ የሆነው፣ በዚሁ ቢዝነስ ነው። በእርግጥ፣ በዚሁ የድለላ ስራ ብቻ ለመቀጠል አይደለም እቅዳቸው።
አፕል፣ ሾፌር አልባ መኪኖቹን፣ ለታክሲ አገልግሎት ያውላቸዋል። ኡበር ኩባንያም አርፎ አልተቀመጠም። እሱም በፊናው፣ ‘ሾፌር ለምኔ’ መኪኖችን ለማምረት፣ አዲስ ኢንቨስትመንት ጀምሯል።
በአጭሩ፣ ግዙፎቹ የኢንተርኔት ኩባንያዎች የመኪና ኢንዱስትሪውን ለመቀላቀል ቆርጠው ተነስተዋል። እንግዲህ፣ ነባሮቹ የመኪና አምራች ኩባንያዎች፣ እነ ቶዮታና እነ ጂኤም ይጨነቁበት እንደሆነ እንጂ፣ መልካም ውጤት እንዲያገኙ ከመመኘት ውጭ ምን ይደረጋል? የቴክኖሎጂ ግስጋሴ፣ ለሁላችንም በጐ እድሎችን ይፈጥራል፡፡ ለእነሱ ሲዘንብ፣ እኛም ቢያንስ ቢያንስ ካፊያ ማግኘታችን አይቀርማ።
ለነሱ ሲዘንብ፣ ለአዳሜ ያካፋል
አፕል፣ በአመት ከሃምሳ ቢሊዮን ዶላር በላይ (ከ1 ትሪሊዮን ብር በላይ ... ማለትም ከኢትዮጵያ አመታዊ የእርሻና የኢንዱስትሪ ጠቅላላ ምርት፣ በእጥፍ የሚበልጥ) ትርፍ እያገኘ ነው። ታዲያ፣ በዋዛ የተገኘ ትርፍ አይደለም፡፡  በመቶ ሚሊዮን የሚቆጠሩ ሰዎች፣ የድንቅ ቴክኖሎጂ ተጠቃሚ እንዲሆኑ በማድረግ ያገኘው ሽልማት ነው።
የአፕልን ቴክኖሎጂ በማየት፣ በአነስተኛ ዋጋ መለስተኛ ስማርት ፎኖችን የሚፈበርኩ ሌሎች ኩባንያዎች በመበራከታቸውም፤ ብዙ መቶ ሚሊዮን የአፍሪካ፣ የቻይና እና የህንድ ሰዎች፣ የቴክኖሎጂ ባይተዋር ከመሆን ድነዋል። ቃል በቃል፣ ቴክኖሎጂው በቢሊዮን ሰዎች እጅ ውስጥ ገብቷል። ቴክኖሎጂው እኛም ጋ ደርሷል፡፡ አካፍቷል፡፡ ለዚያውም፣ ድንቅ ቴክኖሎጂ፣ ለኛም ድንቅ እንደሆነ ለመገንዘብ፣ ሩቅ ድረስ ሄደን ትልቁን ማነፃፀሪያ መመልከት እንችላለን - የአሜሪካው ፔንታጎንን።
እኛ ካፊያ ሲደርሰን፤ ፔንታጐን ምን አገኘ?
የአሜሪካ የመከላከያ ሚኒስቴር (ፔንታጐን),ኧ ከ30 ዓመት በፊት፣ የዘመኑ ምርጥ ኮምፒተሮችን የመጠቀም እድል ነበረው። እንኳን ለአፍሪካ ለአውሮፓም፣ የከዋክብት ያህል እጅግ ሩቅ የነበሩ እነዚያ ‘ምርጥ ኮምፒዩተሮች’፣ በወቅቱ ጉድ ተብሎላቸዋል። አሁን ሲታዩ፣ ... መረጃ የመያዝ አቅማቸውና ፍጥነታቸው አስቂኝ ሊሆንብን ይችላሠ። የዛሬዎቹ ስማርት ፎኖች፣ ከድሮዎቹ ‘ምርጥ ኮምፒዩተሮች’፣ በእልፍ እና እልፍ እጥፍ የሚበልጥ ከፍተኛ አቅም አላቸው።  ናሳ የጠፈር መንኮራኩር በረራ ለመቆጣጠር የገዛቸው ኮምፒዩተሮች፤ ወይም ፔንታጎን ለኒዩክሌር ሚሳየል ማዘዣ ጣቢያ ሲጠቀምባቸው የነበሩ ኮምፒዩተሮች... ዋጋቸው በሚሊዮን ዶላሮች የሚቆጠር ቢሆንም፤ ሺ ኮምፒዩተሮች ተደምረው፣ የአንድ አይፎን ያህል አቅም የላቸውም። ይቅርታ፣ ፔንታጎን “ሲጠቀምባቸው የነበሩ ኮምፒዩተሮች...” የሚለው አገላለፅ ስህተት ነው። እዚሁ ይታማል - በትኩስ መረጃ። ከትናንት በስትያ ረቡዕ እለት፣ ከአሜሪካ መንግስት ዋና ተቆጣጣሪ ቢሮ የወጣ የምርመራ ሪፖርት፣ ስለ ፔንታጎን ኮምፒዩተሮች አስገራሚ መረጃ ይዟል።  ለአገሪቱ ምክርቤት (ለኮንግረስ) የቀረበው የዋና ተቆጣጣሪ ሪፖርት፣ መንግስት ከኮምፒዩተር ጋር ለተያያዙ ስራዎች፣ በዓመት 80 ቢሊዮን ዶላር እንደሚመድብ ይገልፃል። ታዲያ፣ ለአዳዲስ ቴክኖጂዎች የሚውለው ገንዘብ፣ አስር ቢሊዮን ዶላር አይሞላም። እና ሌላኛው 70 ቢሊዮን ዶላር  የት ይገባል? የድሮ ቴክኖሎጂዎችን ለመጠገን!  ብዙ የመንግስት መስሪያ ቤቶች፣ የድሮ ኮምፒዩተሮችን እንደሚጠቀሙ ዋና ተቆጣጣሪው ገልፆ፤ የጡረታ ጉዳዮች ሚኒስቴር፣ ከ30 ዓመት በላይ ባስቆጠሩ የኮምፒዩተር ቴክኖጂዎች እየሰራ መሆኑን በምሳሌነት ጠቅሷል። የታክስ ዋና ዋና መረጃዎች የተከማቹበት የገንዘብ ሚኒስቴር ቴክኖሎጂም፤ የ56 ዓመት አዛውንት እንደሆነ አሶሼትድ ፕሬስ ሐሙስ ዘግቧል። የታላቋ አገር፣ ሃያል የመከላከያ ሚኒስቴር (ፔንታጎን)፣ ከእነዚሁ ዝርዝር ውስጥ መግባቱ ደግሞ ይበልጥ ያስገርማል። የኒዩክሌር ሚሳዬል ማዘዣ መልእክቶችን ለማስተላለፍ፣ ፔንታጎን ውስጥ እያገለገለ የሚገኘው የኮምፒዩተር ቴክኖሎጂ፤ ከ35 ዓመት በላይ ያስቆጠረ የጥንት ኮምፒዩተር ነው። ‘ፋይሎችን’ ለማስቀመጥ፣ ‘ፍሎፒ ዲስክ’ የሚጠቀም የድሮ ኮምፒዩተር፣… ፔንታጎን ውስጥ መገኘቱ አይገርምም? ለዚያውም የኒዩክሌር ሚሳዬል ትዕዛዞችን ለማስተላለፍ የሚያገለግል ኮምፒዩተር! ባለ ‘ፍሎፒ ዲስክ’ ኮምፒዩተር!
“ምን የሚባል ዲስክ?” ብለው የሚጠይቁ ብዙ ሰዎች እንደሚኖሩ እርግጠኛ ነኝ። ዋና ተቆጣጣሪው፣ ፍሎፒ ዲስክ ምን ማለት እንደሆነ በሪፖርታቸው አብራርተዋል።
ፍሎፒ ዲስክ... ከኮምፒዩተር አለም ከጠፋ ስንት ዘመኑ! ፍሎፒ ዲስክ ማለት፤ የድሮ ፍላሽ ዲስክ ወይም፣ የጥንት ሜሞሪ ዲስክ ማለት እንደሆነ በመጠቆም ዋና ተቆጣጣሪው የግርጌ ማስታወሻ ፅፈዋል። 3 ሚሊዮን ፍሎፒ ዲስኮች፤ የአንድ ፍላሽ ዲስክ ያህል አቅም ቢኖራቸው ነው።
ምናለፋችሁ? በኮምፒዩተር ቴክኖሎጂ የመጠቀች አገር ውስጥ፣ በርካታ የመንግስት መስሪያ ቤቶች፣ ፔንታጎንም ጭምር የጥንቱን ታቅፈው ቀርተዋል። ታቅፈው መቅረታቸው ብቻ አይደለም ችግሩ። ወጪያቸው መዓት ነው። መሳሪያዎቹ አርጅተው ነጋ ጠባ ይበላሻሉ። መለዋወጫ እቃ ደግሞ የለም። በኤሌክትሪክ ዘመን የኩራዝ መለዋወጫ፣ በመኪና ዘመን የጋሪ መለዋወጫ እቃ ከየት ይመጣል? በልዩ ትዕዛዝ ለማሰራት ደግሞ... ወጪው የትየሌለ!
የአሜሪካ መንግስት፣ ለኮሙኒኬሽን ቴክኖሎጂ እያለ በየዓመቱ ያን ሁሉ ቢሊዮን ዶላር የሚያፈሰው፤ ‘ያረጀ ጋሪና ኩራዝ’ ለመጠገን ነው ማለት ይቻላል - በታሪክ መዛግብት ብቻ የሚታወቁ የድሮ አሮጌ ኮምፒዩተሮችን ለመጠገን። አሳዛኝ ነው።
አሳዛኝ ቢሆንም፣ በዚህም በዚያም ጠምዝዘን፣ ብለን፣ ‘አወንታዊ’ ትርጉም እንስጠው እንዴ? ‘every cloud has a silver lining’ ይባል የለ! በአወንታዊ ጎኑ ስናየው፤ “እኛ ተመችቶናል፡፡ ፔንታጎን ከሚጠቀምባቸው አንዳንድ ኮምፒዩተሮች ይልቅ፣ በሺ እጥፍ የሚበልጥ ላፕቶፕ ወይም አይፎን እየተጠቀምን ነው” የሚል ትርጉም እናገኛለን። ለኛ፣ የቴክኖሎጂ ካፊያ ደርሶናል፡፡ የሳይንስ፣ የቴክኖሎጂና የቢዝነስ ሰዎች ምስጋና ይድረሳቸውና፤ ሁለት ቢሊዮን የአለም ህዝብ…የስማርት ፎን ተጠቃሚ ሆኗል፡፡ በርካታ የመንግስት መስሪያ ቤቶች ግን፣…ለዚያው በአሜሪካ ጭምር፣ በቴክኖሎጂ ድርቅ ውስጥ አመታትን ይቆጥራሉ፡፡
በሌላ አነጋገር፤ የሆነ ዘመን ላይ ደንዝዞ መቆምና ወደ ኋላ መቅረት፤ መንግስታትን የሚያጠቃ የተለመደ በሽታ ነው። የአሜሪካ መንግስትንም ሳይቀር የሚያጠቃ በሽታ።
መንግስታት በድንዛዜ ወደ ኋላ የሚቀሩት ያለምክንያት አይደለም። ግለሰቦችና የግል ድርጅቶች፣ ከዘመኑ ቴክኖሎጂ ጋር የአቅማቸውን ያህል፣ በትንሽ በትንሹ ጀምረው እየሞካከሩ፣ ጥቅሙንም ቀስ በቀስ እየለመዱ፣ ወደፊት ይጓዛሉ። አለበለዚያ፣ በኪሳራ ከገበያ ይወጣሉ። በመንግስት ቤት ግን፣ መክሰርና ከገበያ መውጣት ብሎ ነገር የለም። ሲከስር፣ ከዜጎች ተጨማሪ ታክስ ይሰበስባል፤ ወይም ገንዘብ ያትማል። ሺ አዳዲስ ኮምፒዩተሮችን ለመግዛት የሚያስችል ገንዘብ፣... የጃጁ ኮምፒዩተሮችን ለመጠገን እያባከነ፤ ለበርካታ አመታት መቀጠል ይችላል። ይሄ በመንግስት ላይ ብቻ ሊከሰት የሚችል በሽታ ነው። ይህም ብቻ አይደለም።
የመንግስት መስሪያ ቤት ውስጥ፣ ብዙ ነገር፣ እንደ አንጀት ረዥም ነው - የተተበተበ ረዥም አንጀት። ቀስ በቀስ፣ አንዱ ከሌላው ልምድ እየቀሰመ ደረጃ በደረጃ ወደ አዲስ ቴክኖሎጂ መሸጋገር፣ ለግለሰቦችና ለግል ድርጅቶች ይሰራል።  በመንግስት መስሪያ ቤት ግን፣ ጣጣው ይበዛል። በየአመቱ እየተከታተለ፣ በጀት እያስፈቀደ፣ ጨረታ እያወጣ... እንደ ራሱ ጉዳይ የሚጣጣር ሰራተኛ ቢኖር እንኳ፣ ብዙም አይራመድም። በሺ እንቅፋት መሃል፣ እየተሽለኮለከ ለማለፍ ሲጣጣር፣ አንድ ሁለት አመት ይሳካለት ይሆናል። ግን፣ ተሰናክሎ መውደቁ የማይቀር ነው። ስለዚህ፣ ሌላኛው አማራጭ፣ሁሉንም ነገር በአንዴ ጠራርጎ፣ በአዲስ ቴክኖሎጂ የመለወጥ ዘመቻ ማወጅ ነው። ይሄስ ያዋጣል?
በአንድ በኩል፣ ‘ቴክኖሎጂው፤ ከፍተኛ ወጪ ይጠይቃል’ እየተባለ፣ ከአመት አመት ይሸጋገራል - አሮጌውን ለመጠገን ብዙ ገንዘብ እያፈሰሰ፤ በድንዛዜ የጥንቱ ቴክኖሎጂ ላይ ተቀርቅሮ ይቀመጣል።
ወይም ደግሞ፣ ወደ አዲስ ቴክኖሎጂ የመሸጋገር ዘመቻ ታውጆ፤ መዓት ገንዘብ ይመደባል። ያው የመንግስት ነገር፤ ብዙ ገንዘብ ስለተመደበ ብቻ፣ ስራው ይሳካል ማለት አይደለም። ስራው ለአመታት ይጓተታል። ብዙ ገንዘብ የወጣበት ገሚሱ ቴክኖሎጂም፣ በትክክል የማይሰራ ሆኖ ያርፈዋል። በኢትዮጵያና እጅና ድሃ በሆነች አገር ውስጥ እንኳ፣ “ወረዳ ኔት”፣ “ስኩልኔት” በሚሉ ስያሜዎች ስንትና ስንት መቶ ሚሊዮን ዶላር ባክኗል፡፡ ግን ይሄ፣ የኢትዮጵያ ባህርይ ሳይሆን፤ የመንግስታት ባህርይ ነው፡፡
(መንግስት ቢዝነስ ውስጥ ሲገባ “ወረፋ ይታጀባል
በሚል ርዕስ የቀረበውን ጽሑፍ ይመልከቱ”)


ግንቦት 20፤ ለኪነ-ጥበቡ አበረከተ የሚባለው ነገር ቅድመ ምርመራን ማስቀረቱ ቢሆንም ቴአትርና ፊልምን ግን ከደርግ ሳንሱር አልተላቀቁም፡፡ ለምሳሌ ሥነ ጽሑፍ፣ ስዕልና ሙዚቃ ቅድመ ምርመራ አይካሄድባቸውም፤ ቀድመው አይታዩም፤ አይመረመሩም፡፡ ይሄ መጽሐፍንም ጋዜጣንም ጭምር ነው፡፡ ፊልምና ቴአትር ግን ይገመገማሉ፡፡ በደርግ ጊዜ የነበረው አሰራር በፊልምና ቴአትር ላይ እስካሁን ቀጥሏል፡፡
ለምሳሌ ቴአትር ለማሳየት ባህልና ቱሪዝም ፈቃድ ካልሰጠሽ ቴአትርሽ አይታይም፡፡ ባህልና ቱሪዝም ፈቃድ ካልፃፈ፣ ክ/ሀገር ሄደሽ ቴአትር ማሳየት አይታሰብም፡፡ ፊልምሽ ሲኒማ ቤት ለመታየት መጀመሪያ መገምገም አለበት፡፡
በአንቺ ስራ ላይ የባህልና ቱሪዝም ሰዎች (ገምጋሚዎቹ) “ይህን ነገር ጨምር፤ ይህንን ነገር አውጣ” የማለት መብት አላቸው፡፡ እስካሁን በግምገማ ምክንያት የታገዱ ምን ምን የመሳሰሉ ቴአትሮችና ፊልሞች አሉ፡፡ “ወይ አዲስ አበባ” የተባለ የጌትነት እንየው ቴአትር በግምገማ ምክንያት ከታገዱት በምሳሌነት የሚጠቀስ ነው፡፡ ይህ ቴአትር ተገምግሞ ታግዷል፡፡ ይህ የሆነው ሊከፈት ለህዝቡ መጥሪያ ከተላከ በኋላ ነው፡፡ ኢህአዴግ ወይም ግንቦት 20፤ ፊልምና ቴአትርን ገና ነፃ አላወጣቸውም፡፡ በቃ ቴአትርና ፊልም አሁንም ባርነት ላይ ናቸው፡፡

(ሰዓሊ ሰይፈ አበበ፣ የኢትዮጵያ ሰዓሊያንና
ቀራፂያን ማህበር ዋና ፀሐፊ)

  በደርግ ስርዓት እኔ ልጅ ነበርኩኝ፤ ሆኖም የደርግ ዘመን ስዕል የሞተበትና በተወሰኑ ሰዎችና በጥቂት ቦታዎች ብቻ ተወስኖ እስትንፋሱ የቆየበት ወቅት ነበር፡፡ እርግጥ በኃይለስላሴ ጊዜ የተከፈተ አቶ አለፈለገ ሠላም የሚባል የስዕል ት/ቤት ነበር፤ ልጅ ሆኜ አባቴ እዛ ልኮኛል፡፡  እኔ በቤተሰብ እውቀትና ስዕል ይወዱ ስለነበር ተላኩ እንጂ ይህን ያህል የተመቻቸ ነገር ኖሮ አልነበረም፡፡ ህብረተሰቡም ለስዕል ትኩረትና አክብሮት ነበረው ለማለት እቸገራለሁ፡፡ “አርፈህ ትምህርትን ተማር” የሚባልበት ጊዜ ነበር፡፡ አርት ት/ቤት ስገባና ኢህአዴግ ሲገባ አንድ ሆነ፡፡ ከግንቦት ሃያ በኋላ በስዕሉ በኩል የመጣው ለውጥ የሚገርም ነው፡፡ ብዙ ጋለሪዎች ተከፈቱ፣ ብዙ እንቅስቃሴ ተጀመረ፡፡ በአሁኑ ወቅት ሰዓሊ ስቱዲዮ ከፎቶ፣ ጋለሪ ከፍቶ ስዕል እየሸጠ የሚኖርበት ጊዜ ነው፡፡ ቱሪስቶች ከውጭ ይመጣሉ፤ በጥሩ ዋጋ ስዕል ይገዛሉ፡፡ ብዙ ጥሩ ጥሩ ነገሮች፤ ምቹ ሁኔታዎች ተፈጥረዋል፡፡ ሰዓሊው በአገር ውስጥም በውጭም የስዕል ኤግዚቢሽኖች የማዘጋጀት፣ ስዕሉን የመሸጥ፣ በስዕል የሚሰማውን የመግለጽ ነፃነት ያገኘው ከግንቦት 20 ወዲህ ነው፡፡ ስርዓቱና አካሄዱ ያመጣው ለውጥ ነው፡፡ እንደምንሰማው ከግንቦት 20 በፊት በነበረው ስርዓት፤ ጥቂት አርት ስኩል የመማር እድል የገጠማቸው ሰዓሊዎች ከተመረቁ በኋላ ሀገር ፍቅር ቴአትር ነው የሚገቡት፡፡ ፖስተር ምናምን ለመስራት ማለት ነው፡፡ እንደ ነጋሽ ወርቁ፣ እነ ጥበበ ተርፋ ያሉ እግዚብሔር የረዳቸው ሰዓሊያን ብቻ… እነ አፈወርቅ ተክሌ ያሉት … በትግል አቆይተውታል፡፡ እነ ገ/ክርስቶስ ደስታም ተሰድደው ህይወታቸውን ያጡበት ጊዜ ነበር፡፡
በአሁኑ ጊዜ እንደ ኤሌያስ ስሜ፣ እነ ዳዊት አበበ፣ ፍቅሩ ገ/ማርያም ያሉ ጐበዝ ጐበዝ ሰዓሊዎች አሉ፡፡ እነ ኤሊያስ ስሜን ብትወስጂ፤ እንደ ኒዮርክ ታይምስና ዋሽንግተን ፖስት ላይ ሽፋን ያገኙ ሰዓሊያን ናቸው ይሄ ግንቦት ሃያ የፈጠረላቸው መልካም አጋጣሚ ነው፡፡ በግንቦት ሃያ፤ ቴክኖሎጂውም አስተሳሰቡም፣ ነፃነቱም አግዞናል፡፡ የኢትዮጵያ ሰዓሊያንና ቀራፂያን ማህበርን መስርተን፤ ህጋዊ ሰውነት አግኝተን እየተንቀሳቀስን ነው፡፡ ይህ ሁሉ የመጣው እንግዲህ በግንቦት 20 ነው፡፡ ሌላው ቀርቶ በአሁኑ ሰዓት የጐዳና ላይ ስዕል ሁሉ ጀምረናል፡፡ ቦሌ መንገድ ላይ መመልከት ይቻላል፡፡ ይህ ስርዓቱ የሰጠን ነፃነት ነው፤ ስለዚህ ለስዕሉ ኢንዱስትሪ ግንቦት ሃያ በርካታ እድሎችን ፈጥሯል ማለት ይቻላል፡፡    

ባለፉት 25 ዓመታት ከምርጫ ጋር ተያይዞ፣ ከተቃውሞ ሰልፍና ውጤታቸው፣ ከፕሬስ ነፃነትና ከጋዜጠኞች ስደት እና እስራት፣ ከብሄር ጎሳዉ ጥቃት እና ከመሳሰሉት ዲሞክራሲያዊ፣
ፍትሃዊና፣ ሰብአዊ ጊዳዮች ጋር በተያያዘ በርካታ አሉታዊ ሪፖርቶች በአለማቀፍ ተቋማት ቀርበዋል፡፡ መንግስት በበኩሉ የሚወጡትን ሪፖርቶች በሙሉ እንደማይቀበላቸው እየተከታተለ
ይፋ ሲያደርግ ከርሟል፡፡ ዲሞክራሲን ስናነሳ ሰብአዊ መብትን ሰብአዊ መብትን ስናነሳ የህግ የበላይነትን፣ የህግ የበላይነትን ስናነሳ ፍትህን እናነሳለን የአዲስ አድማስ ጋዜጠኛ አለማየሁ
አንበሴ የህግ ባለሙያዎችን በዲሞክራሲ፣ በሰብአዊ መብትና በፍትህ ላይ ባለፉት 25 ዓታት ሀገሪቴ ምን ያህል ተራምዳለች ሲል ጠይቋቸዋል፡፡

“ዲሞክራሲ በሌለበት ነፃ ፍ/ቤት ሊኖር አይችልም”    (ዶ/ር ያዕቆብ ኃ/ማርያም፤አለማቀፍ የህግ ባለሙያ)

በሀገራችን እንደ ሰማይ ከራቁ የሰብዓዊ መብቶች ዋነኛው ፍትህ ነው፡፡ አንድ የመንግስት ባለስልጣን ለሰራው ወንጀል ተጠያቂ ያለመሆን በሀገራች ስር የሰደደ ባህል ሆኗል፡፡
ተጠያቂ ያለመሆን ደግሞ ከፍተኛ የፍትህ ጥሰት እንደመሆኑ መጠን፣ በአለማቀፍ ህግ ከፍተኛ አፅንኦት የተሰጠው ጉዳይ ነው፡፡ ዘ ሄግ የሚገኘው አለማቀፍ የህግ ፅ/ቤት የተቋቋመው በዋናነት ተጠያቂነትን ለማስፈን ነው፡፡ የተባበሩት መንግስታት ያቋቋመው የሩዋንዳው ፍ/ቤት የተመሰረተው በዋናነት ሩዋንዳ ውስጥ ተንሰራፍቶ የነበረው የመንግስት ባለስልጣናት ለሰሯቸው ወንጀሎች ተጠያቂ ያለመሆን ባህልን ለመስበር ነው፡፡ ከዚህ አንፃር ስንገመግመው፣ በሀገራችን አንዳንድ ባለስልጣናት ለሰሯቸው ወንጀሎች ተጠያቂ አልሆኑም፡፡ በኢህአዴግ ዘመን ከተቃዋሚዎቹ በስተቀር ከኢህአዴግ ሰዎች ለሰሯቸው ወንጀሎች ተጠያቂ የሆነ የለም፡፡ በወንጀል ተጠያቂ ሊያደርጉ የሚችሉ 3 ምሳሌዎችን መጥቀስ ይችላል፡፡ አንደኛ፤ በ1997 ዓ.ም 300 ሰላማዊ ሰልፈኞች በፀጥታ ኃይሎች መገደላቸውን መንግስት አምኗል፡፡ በጊዜው የደህንነትና የፖሊስ ኃይል፣ በቀድሞው ጠ/ሚኒስትር አቶ መለስ ዜናዊ ቁጥጥርና እዝ ሥር ስለነበረ፣እነዚህ የፀጥታ ኃይሎች ለፈፀሙት ድርጊት አቶ መለስ ተጠያቂ ሲሆኑ አላየንም፡፡
ሁለተኛው፤ኢህአዴግ ኢትዮጵያን ከተቆጣጠረበት ጊዜ አንስቶ ምናልባትም በመቶ ሺዎች የሚቆጠሩ ኢትዮጵያውያን በጎሳቸው ወይም በቋንቋቸው ምክንያት ለዘመናት ከኖሩበት አካባቢ ተፈናቅለው ለከፍተኛ እንግልትና ስቃይ ተዳርገዋል፡፡ ቤኒሻንጉል - ጉራፈርዳን በምሳሌነት መጥቀስ ይቻላል፡፡
ከነዚህ አካባቢዎች የተፈናቀሉት በአብዛኛው አማርኛ ተናጋሪዎች መውደቂያ አጥተው ተንገላተዋል፡፡ አንድን ሰው በዘሩ፣ በሃይማኖቱ፣ በጎሳው ምክንያት ከኖረበት ቦታ ማፈናቀል አለማቀፍ ወንጀል ነው፡፡ በትውልድ ሃገሩ ብቻ ሳይሆን በየትኛውም ሀገር ሆኖ ይህ በደል የደረሰበት ሰው መንግስት ላይ ክስ ሊያቀርብ ይችላል፡፡ ይህ ወንጀል በሰው ፍጡር ላይ የሚፈፀም ወንጀል እንደመሆኑ ክሱ በይርጋ አይታገድም፡፡ ከ20ም ሆነ ከ30 ዓመት በኋላም ቢሆን ክሱን ማንቀሳቀስ ወይም ክስ መመስረት ይቻላል፡፡ ቅጣቱ ብዙ ጊዜ እድሜ ልክ እስራት ነው፡፡ ባለፉት 25 ዓመታት ለዚህ ቅጣት የሚዳርጉ በርካታ ኢ-ሰብአዊ ተግባራት ተፈፅመዋል፡፡ በሦስተኛ ደረጃ በቅርቡ ወደ 400 የሚጠጉ የኦሮሞ ሰላማዊ ወጣቶች ህይወት መጥፋት ተዘግቧል፡፡
 ለዚህ ተጠያቂ የሆነ አካል የለም፡፡ መንግስት ለወንጀሉ ሳይሆን ለድርጊቱ ኃላፊነት ወስዷል፡፡ ለተፈፀመ ድርጊት ይቅርታን በመጠየቅ ወንጀል አይታለፍም፡፡ መንግስት ከተጠያቂነት አሁንም አይድንም፡፡
ለፍትህ ትልቅ ስንቅ የሆኑት አለማቀፍ የሰብአዊ መብት ድንጋጌዎችን የሚንዱ አዋጆች በኢህአዴግ ተደንግገዋል፡፡ ከነዚህ ውስጥ በዋናነት ሊጠቀስ የሚችለው የፀረ-ሽብር አዋጅ ነው፡፡ ይህ አዋጅ የሚደነግጋቸው አንቀፆች ህገ-ወጥ ናቸው፡፡ እንደ ብዙ አውሮፓና አፍሪካ አገሮች፣ ከህገ-መንግስቱ ጋር የሚጣረሱ ህጐችን የሚሽር ነፃ የህገ-መንግስት ፍ/ቤት ቢኖር ኖሮ ይህ አዋጅ በቀጥታ በተሻረ ነበር፡፡ በሀገራችን ይህ ኃላፊነት የተሰጠው የፌደሬሽን ም/ቤት፣ የህገ-መንግስት አጣሪ ጉባኤ ነው፡፡ ይህ አካል የፖለቲካ አካል ስለሆነ ነፃ ነው ለማለት አይቻልም፡፡
ለምሣሌ በ1997 ዓ.ም ተሠናባቹ ፓርላማ፣ ቅንጅት አሸንፎ ሊቆጣጠር ይችላል በሚል ፍራቻ፣ ተተኪውን ፓርላማ ዋጋ ቢስ ያደረገው አዋጅ ይሻርልን ብለን ዶ/ር ሃይሉ አርአያና እኔ ላቀረብነው አቤቱታ መልስ ሳይሰጠን ፋይሉ ተዘግቷል፡፡ ስለዚህ ዲሞክራሲ በሌለበት፣በአንድ ፓርቲ አምባገነንነት በሚተዳደር ሀገር ነፃ ፍርድ ቤት ሊኖር አይችልም፡፡ እስካሁንም ህብረተሰቡ የሚያምነው ነፃ የፍትህ ስርአት አልተገነባም፡፡
 ፕሬስን በተመለከተ በአንዲት ቃል ልጠቅልለው፡፡ በኛ ዘመን የትግሉና የለውጡ ጀግኖች፣ ተማሪዎች ነበሩ፡፡ አሁን ግን ጋዜጠኞች ናቸው፡፡  


===========================

“የሰብአዊ መብት ጥሰት ከጊዜ ወደ ጊዜ እየባሰበት ነው”
(አቶ ተማም አባቡልጉ፤የህግ ባለሙያ

የፍትህ ሥርአቱ ተመስርቷል ወይ ብለን ስንጠይቅ፣ለኔ ገና አልተመሰረተም፡፡ የፍትህ ስርአት ማለት የፖሊስ፣ የፍ/ቤት የአቃቤ ህግና ከነዚህ ጋር ተያያዥ ነው፡፡ የፍትህ ስርአት ተመስርቷል ብለን ስናስብ፣ እነዚህ ተቋማት መኖራቸውን ብቻ ካሰብን ስህተት ነው፡፡ ድሮም ከንጉሱ ጊዜ ጀምሮ እነዚህ ተቋማት ነበሩ፡፡ ፖሊስም ሆነ ፍርድ ቤት ድሮም ነበሩ፡፡ አሁን ማየት ያለብን ከዲሞክራሲ መስፈንና ከህግ የበላይነት አንፃር ነው፡፡
በእነዚህ የፍትህ ተቋማት የዜጎች ሰብአዊና ዲሞክራሲያዊ መብቶች እንዴት እየተከበሩ ነው የሚለው ነው መታየት ያለበት፡፡ የፍትህ ስርአቱ ተቋቁሟል ወይ ስንል፣ ከነዚህ አንፃር ከነጭራሹ አልተቋቋመም፣ የለም፡፡
 ድሮ የነበሩ ስርአቶች አያያዛቸውና መሰረታቸው ይለያያል እንጂ ሁሉም ጨቋኝ ናቸው የሚል ድምዳሜ ነው ያለው፡፡ እነዚህ ስርአቶች በሌላ መልኩ እንዲቀጥሉ ተደረገ እንጂ ሰብአዊና ዲሞክራሲያዊ መብቶችን ከማስከበር አንፃር ብዙ ርቀት አልተሄደም፡፡ ነባሩን ከማስቀጠል በዘለለ አዲስ የፍትህ ስርአት አልተቋቋመም፡፡ የዲሞክራሲ መሰረት የሆነው መድብለ ፓርቲ የሚባለውም በተግባር የለም፡፡ ኢህአዴግ መንግስት ሲሆን ኢትዮጵያን በዘር ነው የከፋፈላት፡፡
 ክልሎቹ በዚህ መንገድ ተሰርተው ካበቁ በኋላ ነው ክልሎቹን ሊያስተዳድሩለት የሚችሉ የብሄር ፓርቲዎችን ያዋቀረው፡፡ የዚህ መሃንዲስ ደግሞ ህወኃት ነው፡፡ ከዚያ በኋላ የመጡ ፓርቲዎች አጃቢዎች ናቸው፡፡ በእኔ ግንዛቤ መድብለ ፓርቲ በኢትዮጵያ እስከ ዛሬ አልተቋቋመም፡፡ የፍትህ ስርአቱም ድሮ ከነበሩት አልተለየም፡፡
ገለልተኛ ምርጫ ቦርድ፣ ገለልተኛ ፍርድ ቤት በሌሉበት መድብለ ፓርቲ ስርአት ሊኖር አይችልም፡፡ የመድብለ ፓርቲ ሥርዓት በሌለበት ስለ ዲሞክራሲ ማውራት አይቻልም፡፡ ኢህአዴግ ከህብረ ብሄራዊ ፓርቲዎች ይልቅ የዘር ፓርቲዎች ነው የሚፈልገው፡፡ የመድብለ ፓርቲ ስርአት በኢትዮጵያ ውስጥ እስካሁን አልተፈጠረም፡፡
የህግ የበላይነት አልሰፈነም የምለው በንጉሱ ዘመን ህግ ነበረ፤ነገር ግን የህግ የበላይነት ከንጉሱ በታች ነው፡፡ ዛሬም ያ ሁኔታ ነው ያለው፡፡ ፍትህ ተአማኒነት እንዲያጣ፣ ሰው ሁሉ የህግ የበላይነት ስህተት እንደሆነ ቆጥሮ፣ ለህግ ክብር እንዲያጣ የተደረገው በዚህ 25 ዓመት  ነው ብዬ አምናለሁ፡፡
የሰብአዊ መብት ጉዳይን ካየን፣ ጥሰቱ ከጊዜ ወደ ጊዜ እየባሰበት ነው፡፡ ደርግ በግልፅ ይገድላል፣ ያስራል፡፡ አሁን ደግሞ ፍርድ ቤት እንደ ሽፋን ያገለግላል፡፡ በእስር ወቅትም ሰላም የለም፡፡
ኢትዮጵያ ውስጥ አሁን ላይ ስርአቱን የነካ ሰው ከሁሉም አቅጣጫ ዱላ ይበዛበታል፡፡ መጠጊያ የለውም፡፡ ፖሊሱ ይጣላዋል፣ አቃቤ ህግ ይጣላዋል፤ ሁሉም ይጣላዋል፡፡ የአባት ገዳይ ተደርጎ ነው የሚታየው፡፡
እንደ ህግ ጠባቂነቴ ያስተዋልኩት፤ዛሬ አንድ ተጠርጣሪ በፖሊስ ሲያዝ መደብደብ፣ መዋከብ የመሳሰሉት ይቅሩ የተባሉ ተግባርት ሁሉ ይፈፀሙበታል፡፡ የድሮው ባህል አልተቀረፈም፤ ድሮም ፖሊስ ሰው ይደበድባል፤ዛሬም ይደበድባል፡፡ ድሮም ተጠርጣሪ በፖሊስ ይመናጨቃል፤ዛሬም ክብሩ አይጠበቅም ይመናጨቃል፡፡
እነዚህን ነገሮች አንስተን ከገመገምን፣ በፍትህና በሰብአዊ እንዲሁም ዲሞክራሲ መመዘኛዎች ኢህአዴግን የሚያህል ፈላጭ ቆራጭ መንግስት ያስተናገድን አይመስለኝም፡፡ ደርግ ወታደራዊ አምባገነን ነበር፡፡ ኃይለሥላሴ ግለሰባዊ አምባገነን ነበሩ፡፡ ኢህአዴግም አምባገነን መንግስት ነው፡፡


======================

“አሁን የተገኘው የፍትህ ሥርአት የ25 ዓመት በረከታችን ነው”
አቶ በሪሁ ተ/ብርሃን (የፌደራል ከፍተኛ ፍ/ቤት ም/ፕሬዚዳንት)

ባለፉት 25 ዓመታት የፍትህ ስርአቱ በተለይ የዳኝነት ስርአቱ ያስመዘገባቸው አጠቃላይ ስኬቶችን ከመናገራችን በፊት የሥርአት ለውጥ ሲመጣ፣ የጥንት ስርአቱም በዚህ ትይዩ ተለውጧል፡፡ የዳኝነት ነጻነትና ተጠያቂነት ህገ መንግስታዊ እንዲሆን በህገ መንግስቱ በግልፅ ከመቀመጡም በላይ የፍ/ቤቶችን ነፃነትና ገለልተኝነት ለማረጋገጥ የህግ ማዕቀፍ ተዘጋጅቶ፣ በዚህ ማዕቀፍ የፍትህ ስርአቱ ሊገነባ መቻሉ፣የ25 ዓመት በረከታችን ነው የሚሆነው፡፡
ሁለተኛው ይሄንን ማረጋገጥ የሚያስችል ቁመና እንዲኖረው የህግ፣ የተቋማዊ ማዕቀፍም የተቀረፀበት ሁኔታ እንዳለ ማየት እንችላለን፡፡ የፍትህ ስርአት አገልግሎቱ በእለት ተእለት ስራው የሚመራባቸው የተለያዩ ህግጋቶች ከመውጣታቸውም ባሻገር እነዚህን ህግጋቶች መሬት ከማውረድ አንፃር በርካታ ተግባራት ተከናውኗል፡፡ የዳኝነት ነፃነት ሊኖር ይገባል የሚለው በህገ መንግስት ብቻ የተወሰነ ሳይሆን የተለያዩ የህግ ማዕቀፎችም ወጥቶለታል፡፡ የዳኝነት ነፃነቱን ሊያረጋግጥና  ዳኝነትን ውጤታማ ሊያደርግ የሚችል ማዕቀፍ ተዘርግቷል፡፡ ሶስተኛ ተቋማዊ ቁመናውን ስንመለከት፣ በፍትህ ስርአቱ የተደረሰበት የተቋም አቅም፣ የሰው ሃብት ልማቱና፣ የዳኞች ምልመላ እንዲሁም የዳኞች የምዘና ስርአት ከቀድሞው ባህል የራቁ ሆነዋል፡፡
በንጉሱ ዘመን የመጨረሻው የፍ/ቤቶች የበላይ የሚሆነው ዙፋን ችሎት ነበር፡፡ አሁን ይሄ የለም፡፡ ችሎቶች ነፃና ገለልተኛ መሆናቸው ብቻ ሳይሆን ከመጀመሪያ ደረጃ - ከፍተኛ - ብሎም ጠቅላይና ሰበር ችሎት ያሉት አደረጃጀቶች፣በራሳቸው ነጻነቱን የጠበቀ የስልጣን ተዋረድ እንዲደራጁ ተደርገዋል፡፡ ለእነዚህ ተቋማት ተመጣጣኝ የሆነ በጀት፣ የሰው ኃይል ተመድቦላቸዋል፡፡ የሰው ኃብት ልማትን ስንመለከት፤ በቅድመ 87፣ 84 በመቶ የሚሆኑት የሀገሪቱ ዳኞች የቤተ ክህነት ምሁራን ናቸው ወይም ከ1-6ኛ የተማሩ ናቸው፡፡ አሁን ግን 97 በመቶ የሚሆኑት ቢያንስ የመጀመሪያ ዲግሪ ያላቸው ናቸው፡፡
ከህግ ጋር ቀጥተኛ ግንኙነት ያለው ባለሙያ በፍትህ ስርአቱ መፈጠሩ ትልቅ እድገት ነው፡፡ እነዚህ ፍርድ ቤቶች ስልጣናቸውና ቁመናቸው የሚመሰረተው በዜጎች ፍትህ ማግኘት ላይ ነው፡፡ ማንኛውም ሰው ፍ/ቤት መቅረብ አለበት ብሎ ያመነበትን የማቅረብ መብት አለው፡፡ በ2008 ዓ.ም ብቻ እንኳ ስንወስድ፣ የፌደራል ፍ/ቤቶች 165ሺህ መዝገቦች በእጃቸው ላይ አለ፡፡ 165ሺህ መዝገቦችን ማስተናገድ መቻል፣ ጉዳዮችን የማስተናገድ አቅማቸው እያደገ መሆኑን አመላካች ነው፡፡ የህግ የበላይነት፤ የህልውና ጉዳይ እየሆነ እንደመጣም ያመላክታል፡፡
ዲሞክራሲና ሰብአዊ መብትን የማስፈን ጉዳይ በህግ የበላይነት የሚመራ እንደመሆኑ፣ ፍ/ቤቶች ተገቢውን ተግባር እየተወጡ ነው፡፡ ፍ/ቤቶች ከህገ መንግስቱ በሚመነጩ ህጎች፤ ዜጎችን እኩል በማስተናገድ ላይ ናቸው፡፡ በሀይማኖት፣ በዘር፣ በፖለቲካ፣ በሀብት፣ በፆታና በመሳሰሉት ልዩነት ሳያደርጉ እያስተናገዱ ነው፡፡ ከዚህ ቀደም “ሰማይ አይታረስ ንጉስ አይከስ” ይባል ነበር፡፡ ለንጉስ ቤተሰቦች ጥበቃ የሚሰጡ በወንጀል ህጉ ላይ በግልፅ የተቀመጡ ድንጋጌዎች የነበሩበት ስርአት አልፈን ነው እዚህ የደረስነው፡፡ በደርግ ጊዜ የሸንጎ ስርአትን በምናይበት ጊዜ በተመሳሳይ የሉአላዊነት ስልጣን ባለቤት የሆነው ሸንጎው ነው፡፡ የህግ የበላይነት ሳይሆን የሸንጎው የበላይነት፣ የዳኝነት የበላይነት ሳይሆን የሸንጎው አስፈፃሚነት የነበረበት ሁኔታ ነበር፡፡ ከዚህ አኳያ ራሱን የቻለ አመርቂ ውጤት መገኘቱን ማየት እንችላለን፡፡
ሌላው ሰብአዊና ዲሞክራሲያዊ መብቶችን ከማክበርና ከማስከበር አኳያ፣ ከሰብአዊ መብት ፅንሰ ሀሳብ ስነሳ፤ እዚህ አገር ዘር የማጥፋት ወንጀል የሚፈፀምበት፣ ያለ ፍርድ የሞት ቅጣት የሚፈፀምበት ነበር፤ የሰው ልጅ ማሰቃየት ተግባር የሚፈፀምበት ሀገር ነበር፡፡ ለምሳሌ እንደ ሂውማን ራይትስዎች ሪፖርት ከሆነ፤ በቀይ ሽብር ጊዜ በ1 ዓመት ውስጥ 500ሺ ኢትዮጵያውያን ያለምንም ፍርድ ተጨፍጭፈዋል፡፡ ይሄን ስናይ ዛሬ ላይ ለኛ የሰብአዊ መብት ጉዳይ የህልውና ጉዳይ ነው፡፡ ያ ታሪክ መደገም ፈፅሞ የለበትም፤ ስለዚህ ሰው የመግደል ወንጀል ብቻ ተብሎ አይታለፍም፡፡ በርካታ ጉዳዮች በፍትህ ይዳኛሉ፡፡ ባለስልጣናት ጭምር ስልጣንን ያለአግባብ ከተገለገሉ ትልቅ ወንጀል ሆኖ ይጠየቃሉ፡፡
በሰብአዊ መብት አያያዝ፣ ከዚህ አንፃር እየተሻሻለ መምጣቱን ማየት እንችላለን፡፡ ፍ/ቤቶች ይሄነ በማክበር፣ በማስከበር የሰብአዊ መብትን የማስጠበቅ ኃላፊነት ያለባቸው መሆኑ ታምኖ እየተሰራበት ነው፡፡ ተከሳሾች ወይም ወደ ፍ/ቤት የቀረቡ ሰዎች፤ ክሳቸውን በግልፅ እያወቁ እንዲከራከሩ፣ የአቃቤ ህግን ማስረጃ የመመልከትና በመረጡት ጠበቃ የመወከል መብት፣ እንዲሁም በሚገባቸው ቋንቋ የመዳኘት መብት አግኝተዋል፡፡ እነዚህን ስራዎች በማጠናከር ቀጣይነት ያለው እየተሻሻለ የሚሄድ ስርአት መፍጠር ያሻል፡፡
ፍ/ቤቶች ባለፉት 25 ዓመታት ውስጣዊ አደረጃጀታቸው እያደገ መሄዱ ብቻ ሳይሆን በአጠቃላይ ለሀገሪቱ ሰላምና መረጋጋት ያበረከቱት አስተዋፅኦ ከፍተኛ ነው፡፡ ፍትህ ለዜጋው እንዲደርስ ያደረጉት አስተዋጽኦም ተጠቃሽ ነው፡፡ ሀገሪቱ እያስመዘገበች ላለው እድገት፤ድጋፍና አጋዥ በመሆን የድርሻቸውን እየተወጡ ነው ማለት ይቻላል፡፡
ይሄን ስንል እጥረቶች የሉም ማለት አይደለም፤ አሉ፡፡ ለምሳሌ ወንጀል የማይሸከም ማህበረሰብ ከመፍጠር አንጻር በሁሉም ባለድርሻዎች ዘንድ ትኩረት ተሰጥቶት ሊሰራበት ይገባል፡፡ ሌላው ወንጀል የሚሰሩ ወገኖችን አቅማቸውን በማዳከም ረገድ እየተሰራ ያለ ቢሆንም የበለጠ ተጠናክሮ መቀጠል አለበት፡፡
የህግ የበላይነትና ዲሞክራሲ በሌለበት መልካም አስተዳደር ስለማይኖር በአፅንኦት ማስፈን ያስፈልጋል፡፡ ሙስናን፣ ስልጣንን ለግል ጥቅም አለማዋል እንዲሁም ኢ-ፍትሃዊ አሰራርን ከመዋጋት አንፃር እያደገ ሊሄድ የሚገባው መሰረት አለ፤ያንን ማጠናከር ያስፈልጋል፡፡ በተለይ ጥራቱን የጠበቀ፣ ወጥነት ያለው፣እየተጠናከረ የሚሄድ ስርአት ለማበጀት፣ የህብረተሰቡ ተሳትፎ በሰፊው ይጠበቃል፡፡ ሂደቱን ፍትሃዊ ለማድረግ የአቅም ችግርና የዳኝነት ክፍተቶች፤ እየጎለበቱና እየዳበሩ መሄድ አለባቸው፡፡ የሰው ሀብት ልማቱ ከሚፈለገው አንፃር ገና ብዙ ሊሰራበት ይገባል፡፡

“ሀገሪቱ በዲሞክራሲና በፍትህ ወደፊት አልተራመደችም”


ባለፉት 25 ዓመታት ሀገሪቱ በዲሞክራሲ፣ በሰብአዊ መብትና በፍትህ የሚጠበቅባትን ያህል ወደፊት አልተራመደችም ሲሉ አንጋፋ የህግ ባለሙያዎች የተቹ ሲሆን የፌደራል ከፍተኛ ፍ/ቤት ም/ፕሬዚዳንት በበኩላቸው፤ በአሁኑ መንግስት ከምንግዜውም የተሻለ የዲሞክራሲ፣ የሰብአዊ መብትና የፍትህ ስርአት ተዘርግቷል ብለዋል፡፡ አንጋፋው የህግ ባለሙያ አቶ አብዱ አሊ ሂጅራ ለአዲስ አድማስ በሰጡት አስተያየት፤ “ዲሞክራሲ ማለት ሃሳብን በነፃነት የመግለፅ መብት ነው፤ በአሁን ወቅት ግን በኢትዮጵያ ውስጥ የሃሳብ ልዩነትን ማስተናገድ የሚችል ስርአት አልተፈጠረም” ብለዋል፡፡
“ዲሞክራሲ በሌለበት ነፃ ፍ/ቤት ሊኖር አይችልም” ያሉት ዓለምአቀፉ የህግ ባለሙያ ዶ/ር ያዕቆብ ኃ/ማርያም በበኩላቸው፤ ወንጀል የሰሩ ከፍተኛ ባለስልጣናት በህግ አለመጠየቃቸውን ጠቅሰው የህግ የበላይነትም እየተከበረ አይደለም ብለዋል፡፡ “ለፍትህ ስንቅ የሆኑ አለማቀፍ የሰብአዊ መብት ድንጋጌዎችን የሚንዱ አዋጆች መፅደቃቸው የፍትህ ስርአቱ ወደፊት እንዳይራመድ አድርጎታል” ሲሉም ተችተዋል፤ ዶ/ር ያዕቆብ፡፡
ሌላው የህግ ባለሙያ አቶ ተማም አባቡልጉ፤ የፍትህ ስርአቱ በሚፈለገው መጠን ገና እንዳልተመሰረተ ገልፀው፤ የፍትህ ተቋማት መኖር ብቻውን ፍትህ አለ አያስብልም ብለዋል፡፡
“የህግ የበላይነት ሠፍኗል ብዬ አላምንም” ያሉት አቶ ተማም፤ የሰብአዊ መብት ጥሰት ከጊዜ ወደጊዜ እየተባባሰ ነው ብለዋል፡፡ የፌደራል ከፍተኛ ፍ/ቤት ም/ፕሬዚዳንት አቶ በሪሁ ተ/ብርሃን በበኩላቸው፤ የስርአት ለውጥ ሲመጣ የዳኝነት ነፃነትና ተጠያቂነት ህገመንግስታዊ እንዲሆን መደንገጉ፣ በፍትህ ስርአቱ ላይ ለውጥ አምጥቷል ብለዋል፡፡
 ዲሞክራሲና ሰብአዊ መብትን የማስፈን ጉዳይ በህግ የበላይነት የሚመራ እንደመሆኑ ፍ/ቤቶች በዚህ በኩል ተገቢውን ተግባር እየተወጡ እንደሆነም ም/ፕሬዚዳንቱ ገልፀዋል፡፡