Administrator

Administrator

ኤጀንሲዎች ህጻናትን እየላኩ ገንዘብ በመሰብሰብ ተጠምደዋል ተብሏል
    የዴንማርክ የማህበራዊ ጉዳዮችና የአገር ውስጥ ሚኒስቴር፤ በኢትዮጵያውያ የሚታየው የጉዲፈቻ አሰራር ያልተገባና ህጻናትን ወደ ውጭ አገራት በመላክ ገንዘብ መሰብሰብ ላይ ያተኮረ መሆኑ በጥናት መረጋገጡን ጠቁሞ፣ ከአሁን በኋላ ኢትዮጵያውያን ህጻናትን በጉዲፈቻ ላለመቀበል መወሰኑን አስታውቋል፡፡
“ዘ ኮፐንሃገን ፖስት” የተባለው የአገሪቱ ጋዜጣ እንደዘገበው፣ በኢትዮጵያ ያለው ህጻናትን በማደጎ ወደ ውጭ አገራት የመላክ አሰራር ዴንማርክ በአለማቀፍ የማደጎ ሂደት የምትከተለውን መርህ የማያሟላ ሆኖ በመገኘቱ ውሳኔው ሊተላለፍ ችሏል፤ ሲል ዘግቧል፡፡
በኢትዮጵያ የሚንቀሳቀሱ የጉዲፈቻ አስፈጻሚ ኤጀንሲዎች ወደ ዴንማርክ የሚልኳቸውን ህጻናት በተመለከተ የሚሰጡት መረጃ በአብዛኛው ወጥነት የሌለው ነው ያለው ዘገባው፣ ኤጀንሲዎቹ ትኩረታቸውን ያደረጉት ከውጭ አገራት ኤጀንሲዎች ገንዘብ በመሰብሰብ ላይ መሆኑንና አገራዊ መፍትሄ ከመሻት ይልቅ ህጻናቱን ወደ ውጭ አገራት በማደጎ በመላክ እንደተጠመዱ ጠቁሟል፡፡ በተጠናቀቀው የፈረንጆች አመት 2015 ብቻ በአለማቀፍ የጉዲፈቻ ቅበላ ሂደት 100 ያህል ህጻናት ወደ ዴንማርክ መግባታቸውን ያስታወሰው ዘገባው፤ ከእነዚህ ህጻናት መካከል ሰባቱ ኢትዮጵያውያን መሆናቸውን አስታውቋል፡፡

በአርባምንጭ ሆስፒታል ከ140 በላይ ህሙማን ህክምና እየተሰጣቸው ነው

     በደቡብ ክልል አርባምንጭ ዙሪያ አማሮና አባያ ወረዳዎች በኦሮሚያ ክልል በቦረና ዞን ገላን ወረዳና በሶማሌ ክልል ሞያሌ ወረዳዎች ላይ የኮሌራ ወረርሽኝ መከሰቱን የጤና ጥበቃ ሚኒስቴር ገለጸ፡፡
ሚኒስቴር መ/ቤቱ ሰሞኑን በሰጠው ጋዜጣዊ መግለጫ ላይ ይፋ እንዳደረገው፤ በሶስቱ ክልሎች በተከሰተው የኮሌራ ወረርሽኝ የሚያዙ ሰዎች ቁጥር እየጨመረ ነው፡፡ በአተት በሽታ የተያዘ ሰው አፋጣኝ ህክምና ካላገኘ የመሞት ዕድሉ ከፍተኛ ነው ያለው መግለጫው፤ህብረተሰቡ በሽታውን ለመከላከል ከፍተኛ ጥንቃቄ ማድረግ ይገባዋል ብሏል፡፡
የአርባ ምንጭ ሆስፒታል ሜዲካል ዳይሬክተር ዶ/ር ቀፀላ ለማ ለአዲስ አድማስ እንደተናገሩት በሽታው በወረርሽኝ መልክ ከተከሰተበት ከአለፈው እሁድ ጀምሮ ከ140 በላይ ህሙማን በዚሁ በሽታ ተይዘው ወደ ሆስፒታሉ መጥተዋል፡፡ ለህሙማኑ የህክምና ማዕከል ተቋቁሞ ዕርዳታ እየተደረገላቸው መሆኑን ዶ/ሩ ገልፀዋል፡፡ በበሽታው ሳቢያ ህይወታቸው ያለፈ ሰዎች ስለመኖራቸው እንደማያውቁ የተናገሩት ዶ/ሩ፤ ወደ ሆስፒታሉ የመጡ ህሙማን ግን ተገቢው ህክምና እየተደረገላቸው በመሆኑ የሞት አደጋ አለመኖሩን ተናግረዋል፡፡  
ከሰሞኑ ዝናባማ የአየር ንብረት ጋር በተያያዘ በሚከሰተው ጐርፍ፤ ምንጮች፣ የውሃ ጉድጓዶችና ወንዞች ስለሚበከሉና ይህም በሽታውን በቀላሉ ለማስተላለፍ የሚችል በመሆኑ ህብረተሰቡ ከፍተኛ ጥንቃቄ ማድረግ ይኖርበታል ያለው ጤና ጥበቃ ሚ/ር፤ ለመጠጥነት የሚውሉ ውሃዎች በአግባቡ ተፈልተውና ቀዝቅዘው አሊያም በውሃ ማከሚያ መድሃኒቶች ታክመው ጥቅም ላይ ሊውሉ እንደሚገባ አሳስቧል፡፡   

   - ቢል ጌትስ በ75 ቢ. ዶላር፣ ዘንድሮም አንደኛ ነው
                 - የፌስቡኩ ዙክበርግ ከፍተኛውን የሃብት ጭማሪ አግኝቷል
                 - ቻይና ዘንድሮ 70 አዳዲስ ቢሊየነሮችን አፍርታለች
    በየአመቱ የዓለማችንን ባለጸጎች የሃብት መጠን በመገምገም ይፋ የሚያደርገው ታዋቂው ፎርብስ መጽሄት፣ ዘንድሮም የተለያዩ አገራት ዜግነት ያላቸው 1ሺህ 810 ባለጸጎች የተካተቱበትን የ2016 የዓለማችን ቀዳሚ ቢሊየነሮችን ዝርዝር ባለፈው ማክሰኞ ይፋ አድርጓል፡፡
የማይክሮሶፍቱ መስራች ቢል ጌትስ የሃብት መጠናቸው ከአምናው የ4.2 ቢሊዮን ዶላር ቅናሽ በማሳየት ወደ 75 ቢሊዮን ዶላር ዝቅ ቢልም፣ ዘንድሮም የፎርብስ የዓለማችን ቀዳሚ ቢሊየነሮችን ዝርዝር በአንደኛነት ከመምራት የሚያግዳቸው አልተገኘም፡፡ እኒሁ ስመጥር ባለጸጋ በሃብታቸው መጠን አለምን ሲመሩ የአሁኑ ለ17ኛ ጊዜ ነው ተብሏል፡፡
ዛራ ፋሽን የተባለው አለማቀፍ የአልባሳት አምራች ኩባንያ ባለቤት የሆኑት ስፔናዊው አማኒኮ ኦርቴጋ፤ በ67 ቢሊዮን ዶላር ሁለተኛ ደረጃን ሲይዙ፣ 60.8 ቢሊዮን ዶላር የተጣራ ሃብት ያላቸው አሜሪካዊው ቢሊየነር ዋረን ቡፌት ሶስተኛ ሆነዋል፡፡ ሜክሲኳዊው የቴሌኮም ዘርፍ ባለጸጋ ካርሎስ ስሊም በ50 ቢሊዮን ዶላር አራተኛ ደረጃ ላይ ሲቀመጡ፣ የአማዞን ኩባንያ መስራችና ዋና ስራ አስፈጻሚ ጄፍ ቤዞስ፣ በ45.2 ቢሊዮን ዶላር አምስተኛው የዓለማችን ቢሊየነር ሆነዋል፡፡
በዘንድሮው የፎርብስ መጽሄት የዓለማችን ቢሊየነሮች ዝርዝር ውስጥ 190 ሴት ቢሊየነሮች መካተታቸውና የወንዶች የበላይነት መግነኑ የታወቀ ሲሆን በ11ኛነት የተቀመጠችውና ከአለማችን ሴቶች በሃብት ቀዳሚውን ስፍራ የያዘችው፣ 36.1 ቢሊዮን ዶላር ያፈራችው የታዋቂው የፋሽንና የመዋቢያ ቁሳቁስ አምራች ኩባንያ ሎሪል መስራችና ባለቤት ፈረንሳዊቷ ሊሊያን ቤተንኮርት ናት፡፡
በአመቱ ዝርዝር ውስጥ 540 ዜጎቿ የተካተቱላት አሜሪካ በርካታ ቢሊየነሮችን በማስመዝገብ ቀዳሚዋ አገር ስትሆን ቻይና በ251፣ ጀርመን በ120፣ ህንድ በ84 እና ሩስያ በ77 ቢሊየነሮች ከሁለት እስከ አምስት ያለውን ደረጃ ይዘዋል፡፡
በ2016 በርካታ አዳዲስ ቢሊየነሮችን በማፍራት ቀዳሚነቱን የያዘቺው ቻይና ስትሆን፣ 70 ባለጸጎቿን በአመቱ የቢሊየነሮች ዝርዝር ውስጥ አካትታለች። በዘንድሮው የፎርብስ ዝርዝር በዕድሜ ለጋዎቹ ባለጸጎች ተብለው የተጠቀሱት ደግሞ፣ የ19 አመቷ የኖርዌይ ተወላጅ አሌክስንድራ አንደርሰንና አንድ አመት የምትበልጣት ታላቅ እህቷ ካትሪና አንደርሰን ናቸው፡፡
ባለፈው አመት 1826 የነበረው የአለማችን ቢሊየነሮች ቁጥር፣ ዘንድሮ ወደ 1810 ዝቅ ብሏል ያለው ፎርብስ፣ ባለፈው አመት ከነበራቸው ሃብት 20.1 ቢሊዮን ዶላር ቅናሽ ያሳዩት ሜክሲኳዊው ቢሊየነር ካርሎስ ስሊም ከፍተኛ ኪሳራ የገጠማቸው ባለጸጋ መሆናቸውንም አመልክቷል፡፡
በአንጻሩ ከአምናው ሃብቱ የ11.2 ቢሊዮን ዶላር የሃብት መጠን ጭማሪ በማስመዝገብ 44.6 ቢሊዮን ዶላር ያደረሰውና በዓለማችን የቢሊየነሮች ዝርዝር ውስጥ ደረጃውን ወደ ስድስተኛነት ከፍ ያደረገው የፌስቡኩ መስራች ማርክ ዙክበርግ፣ በአመቱ ከፍተኛውን የሃብት ጭማሪ ያስተናገደ ባለጸጋ ተብሏል፡፡

     - ድርቁ በአካባቢው በሚገኙ 7 አገራት ተከስቷል
     በሶርያና በምስራቃዊ ሜዲትራኒያን አካባቢ በሚገኙት ቆጵሮስ፣ እስራኤል፣ ዮርዳኖስ፣ ሊባኖስ፣ ፍልስጤምና ቱርክ በአየር ንብረት ለውጥ ሳቢያ የተከሰተው ድርቅ፣ በአካባቢው ያለፉት 500 አመታት ታሪክ የከፋው ሊሆን እንደሚችል መጠቆሙን ዘ ጋርዲያን ዘገበ፡፡
ከአሜሪካ የጠፈር ምርምር ተቋም ናሳ፣ ከኮሎምቢያ ዩኒቨርሲቲና ከአሪዞና ዩኒቨርሲቲ የተውጣጡ ተመራማሪዎች ባደረጉት ጥናት፣ በአካባቢው እ.ኤ.አ ከ1998 ጀምሮ የተከሰተው ድርቅ እየተባባሰ መምጣቱን ማረጋገጣቸውን የጠቆመው ዘገባው፣ ድርቁ በዚሁ ከቀጠለ ባለፉት 500 አመታት የአካባቢው ታሪክ የከፋው የመሆን ከፍተኛ እድል እንዳለው መናገራቸውንም አመልክቷል፡፡
ጆርናል ኦፍ ጂኦፊዚካል ሪሰርች አትሞስፌርስ በተባለ የህትመት ውጤት ላይ ለንባብ የበቃውና የአካባቢውን አገራት የረጅም ዘመናት የአየር ንብረት ሁኔታ በመዳሰስ የተዘጋጀው የተመራማሪዎቹ የጥናት ውጤት እንደሚለው፣ በአካባቢው አገራት የተከሰተው ድርቅ እየተባባሰ እንደሚሄድ ይጠበቃል፡፡ ለድርቁ በምክንያትነት ለተጠቀሰው የአየር ንብረት ለውጥ የበካይ ጋዞች ልቀት ከፍተኛ አስተዋጽኦ እንዳለውና ድርቁ በግጭትና በእርስ በእርስ ግጭት ለሚታመሱት የአካባቢው አገራት ዜጎች ከፍተኛ ፈተና እንደሚሆን መነገሩንም ዘገባው አክሎ ገልጧል፡፡

    የኬንያው ፕሬዚዳንት ኡሁሩ ኬንያታ፤ በአገሪቱ የህዝብ ቁጥርና በፖሊስ ሃይሏ መካከል መመጣጠን ለመፍጠር በማቀድ ተጨማሪ 10 ሺህ አዳዲስ የፖሊስ መኮንኖች እንዲቀጠሩ ለሚመለከተው አካል ትዕዛዝ ማስተላለፋቸውን አፍሪካ ኒውስ ዘገበ፡፡
ፕሬዚዳንቱ ባለፈው ረቡዕ ኢምባካሲ በተባለቺዋ የኬንያ ከተማ ባደረጉት ንግግር፣ የፖሊስ ሃይልን ማጠናከር አገሪቱን ከወንጀል ድርጊቶችና ከወንጀለኞች የጸዳች ለማድረግ የሚጫወተውን ወሳኝ ሚና ከግምት ውስጥ በማስገባት ተጨማሪ የፖሊስ መኮንኖችን ለመቅጠርና ወደ ስራ ለማሰማራት መወሰናቸውን ተናግረዋል፡፡
የአገሪቱ የፖሊስ መኮንኖች አገራቸውን ከወንጀል ድርጊቶች ለመከላከል በቁርጠኝነት እንዲሰሩ ጥሪያቸውን ያስተላለፉት ኡሁሩ ኬንያታ፣ መንግስታቸው ከዚህ በፊት ያደርገው እንደነበረው ሁሉ የፖሊስ አባላትን የአኗኗር ሁኔታ ለማሻሻል መስራቱን እንደሚቀጥልም ገልጸዋል፡፡
የኬንያ ብሄራዊ የፖሊስ አገልግሎት ኮሚሽን የፕሬዚዳንቱን የፖሊስ ሃይል የማጠናከር አገር አቀፍ እቅድ ለማስፈጸም እየተዘጋጀ እንደሚገኝ የጠቆመው ዘገባው፣ በተቀመጠው መስፈርት መሰረት የሚመለመሉት 10 ሺህ የፖሊስ መኮንኖችን በአንድ አመት ጊዜ ውስጥ ስልጠናቸውን አጠናቀው ወደ ስራ ይገባሉ ተብሎ እንደሚጠበቅም ጠቁሟል፡፡

    የአሜሪካው የጠፈር ምርምር ተቋም ናሳ በቅርቡ ላወጣቸው 8 የተለያዩ ክፍት የስራ ቦታዎች ማስታወቂያ፣ 18 ሺህ 300 ያህል አመልካቾች መመዝገባቸውንና ይህም በተቋሙ ስራ ለማግኘት በርካታ አመልካቾች የቀረቡበት የመጀመሪያው ክስተት ሆኖ መመዝገቡን ስካይ ኒውስ ዘገበ፡፡
ለክፍት የስራ ቦታዎቹ ያመለከቱት ሰዎች በዚህ መጠን ለመብዛታቸው እንደ ምክንያት ከተጠቀሱት ጉዳዮች መካከልም ማህበራዊ ድረገጾች የስራ ማስታወቂያዎችንና የቅጥር አገልግሎቶችን ማስፋፋታቸው እንዲሁም በጠፈር ጉዞ ላይ ያለው ፍላጎት እየጨመረ መምጣቱ ይገኙበታል፡፡
በተቋሙ ታሪክ እጅግ ፉክክር የበዛበት ይሆናል ተብሎ በሚጠበቀው በዚህ የቅጥር ሂደት፣ በመስፈርትነት የተቀመጡትን የዜግነትና የትምህርት ደረጃ ሁኔታዎችን ያላሟሉ አመልካቾች ወዲያውኑ ከውድድር ውጭ ይደረጋሉ ተብሎ ይጠበቃል ተብሏል፡፡ ናሳ ላወጣቸው ክፍት የስራ ቦታዎቹ መቅጠር የሚፈልገው አሜሪካውያንን ብቻ እንደሆነና በምህንድስና፣ በባዮሎጂካል ሳይንስ፣ በፊዚካል ሳይንስና በሂሳብ ወይም በኮምፒውተር የትምህርት መስኮች ቢያንስ የመጀመሪያ ዲግሪ ያላቸውን እንደሆነ ተነግሯል፡፡
የጠፈር ምርምር ተቋሙ እ.ኤ.አ በ1978 ላወጣቸው ክፍት የስራ ቦታዎች 8 ሺህ አመልካቾች የቀረቡበት አጋጣሚ ከፍተኛ ቁጥር ያላቸው አመልካቾች የቀረረቡበት ሆኖ ተመዝግቦ እንደነበርም ዘገባው አስታውሷል፡፡

ከኤዞፕ ተረቶች አንዱ እንዲህ ይላል፡-
ከዕለታት አንድ ቀን፣ አንዲት የተራበች ቀበሮ፣ በአንድ ውስጡ ባዶ በሆነ ግንድ ውስጥ እየኖረች ከመንገድ ሲመለሱ ሊበሉት ያስቀመጡትን ዳቦና ስጋ ታገኛለች፡፡
በጣም እየተስገበገበች እዚያ የተቦረቦረ የግንድ ስንጥቅ ውስጥ ገብታ እንደ ጉድ ትውጠው፣ ትሰለቅጠው ገባች፡፡ ያንን ዳቦና ስጋ በላች በላችና ሆዷ እንደ ከበሮ ተነረተ፡፡ አስቀድማ በቀላሉ ገብታበት የነበረችው ቀዳዳ አሁን በጭራሽ የሚሞከር አልሆነም፡፡ ሆዷን ብትጨምቀው እጅ እግሯን ብታጥፈው በምንም ዓይነት ለመውጣት የምትችልበት ዘዴ ጠፋ፡፡ በምሬት እየተንሰቀሰቀች፤
“አወይ የክፉ ቀን
አወይ የአበሳ ቀን
መከራው መርዘሙ
እንኳን መወፈሩ ያቅታል መክሰሙ
የገቡበት በራፍ
አርቡ ጠቦ ጠቦ
አላሳልፍ ይላል መውጫውን ገድቦ!”
ቀበሮ እንዲህ እያለች ስታለቅስና ዕጣ - ፈንታዋን ስታማርር፤ በአጋጣሚ በዚያው ግድም የሚያልፍ አንድ ቀበሮ፤ “ምን ሆነሽ ነው የምታለቅሺው እመት ቀበሮ?” ሲል ይጠይቃታል
እመት ቀበሮም፤
“ሳይቸግረኝ እዚህ ግንድ ውስጥ ገብቼ፣ የእረኞቹን ስንቅ በልቼ በልቼ ሆዴ ተነፍቶ፣ ሰውነቴ ተወጣጥሮ በጭራሽ ከገባሁበት መውጣት አቃተኝ፡፡ ምን እንደማደርግ መላው ሲጠፋኝ፣ ይሄው እያለቀስኩኝ አምላኬን አውጣኝ ብዬ በእንጉርጉሮ እለምናለሁ፡፡”
አያ መንገደኛ ቀበሮም፤
“የእረኞቹን ስንቅ መብላትሽ ደግ አላደረግሽም፡፡ የሰው ንብረት መውሰድ ምን ጊዜም ዋጋ ያስከፍላል፡፡ መፀለይ ያለብሽ እረኞቹ ከሄዱበት በቶሎ እንዳይመለሱ ነው፡፡ ያ ካልሆነ እዚያው ባለሽበት ቆዪ፡፡ ወደ ዱሮው ከሲታ አካላትሽ ትመለሺያለሽ፡፡ ከዚያ ትወጫለሽ” ብሏት መንገዱን ቀጠለ፡፡
*   *   *
የሰው ንብረት መዝረፍም፣ ማስዘረፍም ዋጋ ያስከፍላል፡፡ አንዴ ከተቆዘሩበት በቀላሉ ከስቶ ወደነበሩበት መመለስ የአንድ ጀምበር ጉዳይ አይደለም፡፡ ይዋል ይደር እንጂ የህዝብ ዐይን ማንንም ከተደበቀበትም ይሁን ከተኮፈሰበት ሥፍራ መንጥሮ ያወጣዋል፡፡ መረብም ካለ ቋጠሮው መፈታቱ አይቀርም! “አንተ፤ ብሳና ይሸብታል ወይ?” ብሎ ቢጠይቀው፤ “ለዛፎች ሁሉ ያስተማረው ማን ሆነና?” የሚለው የሩሲያውያን አነጋገር ትልቁንም ወንጀለኛ ትንሹንም ወንጀለኛ፣ ድሮውንም ሙልሙሉንም፣ እንድናይ ያግዘናል፡፡ አለቃም ሆነ ምንዝር ተጠያቂነት ሊዳስሰው ይገባል፡፡ በሀገራችን በተደጋጋሚ ከታዩት ችግሮች አንዱ ሰሞነኛነት ነው፡፡ ለአንድ ሰሞን ዘመቻ ማጧጧፍ! ለአንድ ሰሞን ዘራፍ ማለት! ቆይቶ ሁሉንም መርሳት! ወንጀል ይሥሩም አይሥሩም የፊተኞቹ ብቻ “ሰለባ” ሆነው ይቀራሉ፡፡ ይህን አባዜ መገላገል አለብን፡፡ ፍትህ ዘላቂ ጎዳና ላይ መውጣት አለበት፡፡ እንደ ውሃ ማቆርም የአንድ ሰሞን ዜና መሆን የለበትም፡፡ የአገር ጉዳይ “ፉርሽ ባትሉኝ!” የሚባልበት የልጆች ጨዋታ አይደለም፡፡ የሚወሰዱ እርምጃዎች አመርቂ መሆን አለባቸው፡፡ ለውጥ መምጣት ካለበት በአገም ጠቀም አይሆንም፡፡
ደራሲ ተክለፃዲቅ መኩሪያ ስለግል ታሪካቸው ሲፅፉ፤ እግረ - መንገዳቸውን ስለ አፄ ኃይለ ሥላሴ ሹማምንት ያነሳሉ፡፡ ከነዚህ መካከል የፀሀፊው ትዕዛዝ ወልደጊዮርጊስን ከሥልጣን መገለል ሲናገሩ እንዲህ ይላሉ፡-
“የበላይ ያደባይ ነውና፤ ፀሐፊ ትዕዛዙ ተዋርደው፤ ግማሽ ሹመት፣ ግማሽ - ግዞት ተደርጎላቸው፣ ወደ አርሲ ተላኩ፡፡”
አካሄዱ ጊዜው የፈቀደው ሆኖ ሊሆን ይችላል፡፡ ዛሬ “ግዞት” ቃሉም ጠፍቶ ሳይሆን አይቀርም፡፡ “ግማሽ - ሹመት ግማሽ - ግዞትም” በረቂቅ ዘዴ ካልሆነ ለሃያ አንደኛው ክፍለ ዘመን ማገልገሉ አጠራጣሪ ነው! መልካም አስተዳደር መልካም አስተዳዳሪ ይፈልጋል፡፡ በስልጣን የሚመኩ መልካም አስተዳዳሪ ሊሆኑ አይችሉም፡፡ “ብቆጣም እመታሻለሁ፣ ብትቆጪም እመታሻለሁ” ዓይነት ዕብሪት ያለባቸው ሹማምንት፤ መልካም አስተዳደር ሊያሰፍኑ ከቶም አይችሉም፡፡ “ሲሾም ያልበላ ሲሻር ይቆጨዋል” የሚሉ ከመልካም አስተዳደር ሩቅ ናቸው፡፡ በጥበትም ይፈረጁ በትምክህት ቀናነት የሌላቸው መልካም አስተዳደርን  አይወርሱም፡፡ አያወርሱም፡፡ ኩራትና ትዕቢት የመልካምነት ፀር ናቸው!
ደራሲ ከበደ ሚካኤል ስለ እንደነዚህ ዓይነት ባለሥልጣናት ሲገጥሙ እንዲህ ይሉናል፡-
“ኩራትና ትዕቢት የሞሉት አናት
ሰይፍና ጎራዴ የመቱት አንገት
አይገላገሉም እንዲህ በቀላሉ
እመሬት ላይ ወድቀው ሳይንከባለሉ!!”
ዕውነትም ዛሬ መሬት መንከባለያ ሆኗል፡፡ የመሬት አስተዳደር ዓይነተኛ መጠያየቂያ ፈተና፤ ዋና ጉዳይ ሆኗል፡፡ በመሬት ዙሪያ የሚፈፀመው ሙስና ደሀውን ያስለቀሰ፣ ጌታውን ያለቅጥ ያስፈነጠዘ፣ የምዝበራዎች ሁሉ ጉልላት ነው፡፡ በሀገራችን የመሬት ኢ-ፍትሐዊ ብዝበዛ ጉዳይ ዛሬ ሳይሆን ትላንት ከትናንት በስቲያ ፈጦ ናጦ ወጥቷል” “በሕግ አምላክ!”፣ “የመንግስት ያለህ!” እያልን ስንጮህበት የነበረ ነው፡፡ በርካታ ሹሞች ከሥልጣን ወደ ሌላ ሥልጣን እየተዛወሩ ሽፋን ያገኙበት ነው፡፡ ላጠፉት ይጠየቃሉ ሲባል ሌላ ሹመት የወረሱበት ነው፡፡ አሁን እየተወሰደ ያለው እርምጃ ለኢትዮጵያ አልረፈደም፡፡ ተመስገን የሚባል ነው፡፡ ሙስና እንደ ናይጄሪያ፣ እንደ ኬንያ፣ አልናጠጠብንም ብሎ መፅናናትም ያባት ነው፡፡
ይህ ማለት ግን በዚያ መንገድ ላይ አይደለንም ማለት አይደለም፡፡ ካልገደብነው እነዚያ አገሮች የደረሱበት የማንደርስበት፣ አልፈንም የማንሄድበት አንዳችም ምክንያት አይኖርም፡፡ “እናቴ፤ በእንቁላሉ ጊዜ በቀጣሽኝ በሬ ሰርቄ ባልታሰርኩ” ያለውን ሰው ልብ ብሎ ማሰብ ብቻ ነው የሚያስፈልገው፡፡
“ሞኞች ናቸው
ዳኞች ሞኞች ናቸው
ዋስ ጥራ ይላሉ
ከነዋሱ ቢሄድ፣ ማንን ይይዛሉ፡፡”
የሚለውን የቀረርቶ ግጥም አለመዘንጋትም ብልህነት ነው! አንድ መሰረታዊ ጉዳይ ግን አለመርሳት ዋና ነገር ነው፡፡ ይኸውም ዛሬ እጃቸው በሙስና ውስጥ ተነክሮ ያሉ አለቃና ምንዝሮች እንደምን ለሥልጣን በቁ? እንደምን አለቃ ሆኑ? ሿሚና አስሿሚ፣ ዕድገት ሰጪና ተሰጪ ምን ሰንሰለት አላቸው? እከክልኝ ልከክልህ ምን ሚሥጥር አለው? ይሄን መፈተሽ ተገቢ ነው፡፡ “አስወርተህ ሹመኝ፣ ዘርፌ አበላሃለሁ” የሚለው ተረት ትልቅ ቁምነገር እንዳለው የምናየው እዚህ ላይ ነው!!

ባለፈው ሰኞ የታክሲ አሽከርካሪዎች በ2003 ዓ.ም ፀድቆ በቅርቡ በተግባር ላይ የዋለውን “የመንገድ
ትራፊክ ደህንነት ደንብ በመቃወም የስራ ማቆም አድማ ማድረጋቸው ይታወሳል፡፡ ማክሰኞ ዕለትም
በተለይ ጠዋት ሙሉ ለሙሉ ሥራ አልጀመሩም ነበር፡፡ የአሽከርካሪዎቹ አድማ ከመደረጉ ሁለት ቀናት
ቀደም ብሎ የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር የደንቡን ተፈፃሚነት ለሶስት ወር ማራዘሙን ማስታወቁ
ይታወሳል፡፡ ደንቡ ለ3 ወር የተራዘመው ለምንድን ነው? የታክሲ አሽከርካሪዎች እንደጠየቁት ደንቡ
ይሻሻል ይሆን? የአዲስ አድማስ ጋዜጠኛ ናፍቆት ዮሴፍ ጠመንገድና ትራንስፖርት ቢሮ ሀላፊ አቶ
ያብባል አዲስን በእነዚህና ተያያዥ ጉዳዮች ዙሪያ አነጋራቸዋለች፡፡

    በ2003 ዓ.ም የፀደቀው የትራፊክ ደህንነት ደንብ ተፈፃሚ የሆነው ዘንድሮ (ሰሞኑን) ነው፡፡ ከአምስት አመታት በኋላ ተፈፃሚ እንዲሆን የተወሰነው በምን ምክንያት ነው?
ደንቡ ሥራ የጀመረው በ2003 ዓ.ም እንደወጣ ሰሞን እንጂ አሁን አይደለም፡፡ ሰሞኑን የተጀመረው የደንቡን ተግባራዊነት ይበልጥ የሚያጠናክር ሥርዓት ነው፡፡ ደንቡማ አገር አቀፍ በመሆኑ ከ2003 ዓ.ም ጀምሮ በአዲስ አበባም በሌሎች ክልሎችም ተግባራዊ ሲሆን ቆይቷል፡፡ የትራፊክ ደንብ ተላላፊዎችም በደንቡ መሰረት ሲቀጡ ቆይተዋል፡፡ ያን ጊዜ ሲቀጡ አይመዘገብምም፤ መረጃ አይወሰድም ነበር፡፡ ቅጣቱም የጥፋት ድግግሞሽን መሰረት ያደረገ አልነበረም፣ አሁን ግን አንድ አሽከርካሪ ደንብ ተላልፎ ሲቀጣ ይመዘገባል፡፡ አሽከርካሪው ዛሬ ሲያጠፋ ይቀጣል፤ ዳግም ሲያጠፋ በየጥፋቱ መጠን ከበድ ያለ ቅጣት ይቀጣል፡፡ እንዲህ እንዲህ እያለ የአሽከርካሪው ጥፋት ገደቡ ላይ ሲደርስ መንጃ ፈቃድ ሊነጠቅ ይችላል፡፡
ደንቡ ሰሞኑን መተግበር ሲጀምር ግን የታክሲ አሽከርካሪዎችን እስከማስቆጣት ብሎም እስከ ስራ ማቆም አድማ አድርሷል፡፡ በሌላ በኩል መንግስት የደንቡን ተፈፃሚነት ለሶስት ወራት ማራዘሙን ገልጿል፡፡ የመንገድ ደህንነት ደንቡ ለምን ተራዘመ? ደንቡን ለማሻሻል ታስቧል?
እንግዲህ ለ3 ወራት የተራዘመበት ዋና ምክንያት ታክሲ አሽከርካሪዎች አንዳንድ ቅሬታዎችን በማንሳታቸው ነው፡፡ አሽከርካሪዎቹ 24 ሰዓት ስለምንሰራ የቅጣት ድግግሞሹ ተመዝግቦ ከተያዘና ተግባራዊ ከሆነ የጥፋት ሪከርዳችን ስለሚበዛ በአንድ ጊዜ መንጃ ፈቃዳችንን እንድንቀማ ያደርጋል፤ ይሄ ደግሞ እኛንም ከስራ ውጭ ያደርጋል፤ ቤተሰቦቻችንም ለችግር ይዳረጋሉ። የጥፋት ድግግሞሻችን እንዳይበዛ አንዳንድ ተጨባጭ ሁኔታዎች መስተካከል አለባቸው ብለው በውይይታችን ወቅት አንስተዋል፡፡
ተጨባጭ  ሁኔታዎች ሲሉ ምን ማለታቸው ነው?
አንደኛ ህብረተሰቡ በጉዳዩ ላይ ግንዛቤ መውሰድ አለበት፡፡ ደንቡም ተፈፃሚ መሆን ያለበት በአሽከርካሪዎች ላይ ብቻ ሳይሆን በህብረተሰቡም ላይ መሆን አለበት፡፡ ሁሉም ባለድርሻ አካል  ሃላፊነቱን እንዲወጣ ግንዛቤ ሊፈጠርለት ይገባል። አሽከርካሪው ብቻ ተገንዝቦት ሌላው አካል ካላወቀው በአንድ እጅ እንደማጨብጨብ ነው። እኛም የምናጠፋው ጥፋት እየበዛ ይመጣል፤ ለምሳሌ እግረኛው የእግረኛ መንገድን ይዞ ካልተጓዘ፣ ዜብራ መንገድ ላይ ለማቋረጥ ፈቃደኛ ካልሆነና ባገኘው መንገድ ላይ የሚያቋርጥ ከሆነ የእኛን ጥፋት እያበዛው ይሄዳል፡፡ ስለሆነም ሰፊ የግንዛቤ ስራ ሊሰራ ይገባል … የሚል ሃሳብ አንስተዋል። ሁለተኛው ለተሽከርካሪዎች በቂ የሆነ ምልክትና የማመላከቻ ስራዎች በየመንገዱ ሊተከል ይገባል ብለዋል፡፡ በሶስተኛነት ለታክሲዎች መቆሚያና ማውረጃ የሚሆኑ ተርሚናሎችን ማዘጋጀት ያስፈልጋል፤  በተጨማሪም ታሪፉ አዋጭ ስላልሆነ ሊሻሻልልን ይገባል፤ እነዚህ ቅድመ ሁኔታዎች ባልተሟሉበት የተፈጠረው ስርዓት እኛን ከገበያ ያስወጣናል ሲሉ በአጽንኦት ተናግረዋል፡፡ የደንቡ ተግባራዊነት ለ3 ወር የተራዘመውም በዚህ ጊዜ ውስጥ በመንግስት ደረጃ ሊሰሩ የሚገባቸውን ቅድመ ዝግጅቶች ለመስራትና በሁሉም ህብረተሰብ ዘንድ የተሟላ ግንዛቤ ለመፍጠር ነው፡፡
በአሽከርካሪዎች የተነሱት ቅድመ ሁኔታዎች በሶስት ወር ጊዜ ውስጥ ተሟልተው ይጠናቀቃሉ ብለው ያስባሉ?
እንግዲህ በአጭር ጊዜ የሚጠናቀቁት ይጠናቀቃሉ፤ ለምሳሌ የግንዛቤ ስራው፣ ይተከሉ የተባሉት ምልክቶችና መሰል ስራዎች ቶሎ ቶሎ ሊሰሩ ይችላሉ፡፡ ቀሪዎቹና ረዘም ያለ ጊዜ የሚጠይቁት ደግሞ ታክሲዎቹ ሥራቸውን እየሰሩ የሚስተካከሉ ይሆናሉ ማለት ነው፡፡
ሰሞኑን ያነጋገርናቸው አድማ ያደረጉ የታክሲ አሽከርካሪዎች ህጉ ለ3 ወር ቢራዘምም ካልተሻሻለ ለህብረተሰቡም ለአሽከርካሪዎችም አስቸጋሪ ነው፤ መሻሻል አለበት ብለዋል፡፡ መንግስት በዚህ ዙሪያ ምን ያሰበው ነገር አለ?
ቀደም ሲል እንደተናገርኩት ደንቡ አገር አቀፍ ደንብ ነው፤ በአማራ ክልል፣ በደቡብና ሌሎች ቦታዎች ተግባራዊ መሆን ከጀመረ ቆይቷል፡፡ ይሄ የቅጣት ድግግሞሽ ምዝገባና የመንጃ ፈቃድ መነጠቁ ጉዳይ ተግባራዊ ሳይሆን የቆየው በአዲስ አበባና በኦሮምያ ብቻ ነው፡፡ እንግዲህ መሻሻል አለበት ወይ? ለሚለው፣ መንግስት ከባለ ድርሻ አካላት ጋር በሰፊው ተወያይቶ መሻሻል ያለበት ነገር ካለ ፌደራል መንግስት የማያሻሽልበት ምክንያት የለም፡፡ ይሄ የመጽሐፍ ቅዱስ ቃል አይደለም፡፡ በግልጽ ተወያይተን አስተካክሉ የተባለውን ጉዳይ ተቀብለነዋል፡፡ እንደነገርኩሽ ችግሩን በአጭር፣ በመካከለኛና በረጅም ጊዜ ለመፍታት ዝግጁ ነን፡፡
ውይይቱ የተካሄደውና አሉ የተባሉ ችግሮች የተነገራችሁ ደንቡ ተግባራዊ ከመሆኑ በፊት ነው። ችግሮቹ ደንቡን ተግባራዊ ከማድረጋችሁና የስራ ማቆም አድማው ከመምጣቱ በፊት ለምን አልተፈቱም?
ችግሮቹ በሂደት እንደሚፈቱና መንግስት በጉዳዩ ላይ ትኩረት ሰጥቶ እየተንቀሳቀሰ መሆኑን ተማምነናል፡፡ በነገራችን ላይ አንድ አገር ላይ ደንብ ሲወጣ ደንቡ ሁሉንም ሊያስደስት አይችልም፡፡ ሆኖም ደስተኛ ያልሆነው አካል ሥራውን እየሰራ ቅር የተሰኘበትን ነገር መጠየቅ ይችላል፡፡ ምክንያቱም ማንኛውም ሰው ከህግ በታች ነው፡፡ አሽከርካሪዎች ሙሉ ለሙሉ ሥራ ማቆማቸው አግባብ አይደለም፤ በአገር ኢኮኖሚም ሆነ በማህበረሰቡ ላይ የሚያደርሰው ጉዳት ከፍተኛ ነው፡፡
ባለፈው ሰኞ የስራ ማቆም አድማው ሲደረግ የትራንስፖርት ተቆጣጣሪዎች ለስራ የወጡትን ታክሲዎች ታርጋ ሲመዘግቡና በአድማው በተሳተፉት ላይ እርምጃ እንደሚወሰድ ሲናገሩ ሰምተናል፡፡ ባልተሰማሩት ላይ ምን እርምጃ ተወሰደ? በአድማው ዕለት ምን ያህሉ ስራ ላይ ነበሩ?
በአዲስ አበባ ውስጥ ኮድ አንድና ኮድ ሶስት የሚባሉ ታክሲዎች አሉ፤ በአጠቃላይ ቁጥራቸው 10ሺህ አካባቢ ነው፡፡ ከነዚህ መካከል በአድማው ዕለት ስራ ላይ የነበሩት  ከ1500 አይበልጡም ነበር፡፡ ታክሲዎች ሙሉ ለሙሉ ሥራ አቁመው ነበር ማለት ይቻላል፡፡ ይህ ደግሞ ያስከተለው ኢኮኖሚያዊና ማህበራዊ ቀውስ ቀላል አይደለም፡፡ ምን እርምጃ ወሰዳችሁ ላልሽው መንግስት ከቅጣት ይልቅ ማስተማርን ያስቀድማል፤ ከማስጠንቀቅ ውጭ አድማ በመቱት ላይ ምንም እርምጃ አልወሰድንም፡፡     
የደንቡ ተፈፃሚ መሆን በማህበረሰቡና በአሽከርካሪዎቹ ዘንድ እንደ ትልቅ ስጋት  ታይቷል። ብልሹ አሰራርንና ሙሰኝነትን ያስፋፋል የሚል አስተያየት ይሰነዘራል፡ አንድ አሽከርካሪ ለስድስት ወር ወይም ለሁለት ዓመት መንጃ ፈቃዱን ከሚቀማ ከትራፊክ ፖሊሱ ጋር መደራደርንና ገንዘብ መስጠትን ይመርጣል… የሚል ስጋት በስፋት ይንፀባረቃል፡፡ ቢሯችሁ ስጋቱን እንዴት ያየዋል? ይሄንን ለመቆጣጠርስ ምን አይነት ስልት አዘጋጅቷል?
ሥጋቱ የለም ለማለት አይቻልም፡፡ ሙሰኛ ትራፊክም የለም ለማለት ይከብዳል፡፡ አብዛኛውን ህጋዊ የትራፊክ ፖሊስ ባይመለከትም፡፡ በነገራችን ላይ የደንቡ ዋነኛ አላማ እየተባባሰ የመጣውን የትራፊክ አደጋ እንዲሁም በህይወትና ንብረት ላይ እየደረሰ ያለውን ጥፋት ለመቀነስ ነው፡፡ ደንቡ በዚህ መንገድ መታየት አለበት፡፡ ከዚያ አልፎ ደንብ እየተላለፈ ብዙ ስህተት የሚሰራ አሽከርካሪ፤ ከስንቱ ትራፊክ ፖሊስ ጋር ተደራድሮ ይችለዋል? አቅሙም አይፈቅድም፡፡ አንድ ቦታ ላይ አጥፍቶ ለአንድ ትራፊክ ጉቦ ቢከፍል ካልተጠነቀቀ ሌላም ምግባረ ብልሹ የትራፊክ ፖሊስ ሊያጋጥመው ይችላል፡፡ ከዚህ ሁሉ የሚሻለው ደንብና ስርዓቱን አክብሮ ማሽከርከር ነው፡፡ አንዳንድ ምግባረ ብልሹ የትራፊክ ፖሊሶችም የቱንም ያህል ቢጠነቀቁ ከህግ አይን አያመልጡም፤ ከነሱም በላይ እነሱን መቆጣጠሪያ ስልቶች አሉ፡፡ ነገር ግን አሽከርካሪውም ሆነ እግረኛውም እንዲሁም ህግ አስከባሪው አካል ሃላፊነታቸውን ተወጥተው ቢሰሩ የሰው ህይወትም የንብረት ጥፋትም ይቀርና አገር በኢኮኖሚም በማህበራዊም ጐን ታድጋለች፡፡
አንዳንድ የታክሲ ባለንብረቶች ሹፌሮቻቸው አድማ አድርገው ታክሲያቸውን ግቢያቸው ስላቆሙ ብቻ ታርጋ እንደተፈታባቸውና በዚህም ማዘናቸውን ተናግረዋል፡፡ ይህስ አግባብ ነው ይላሉ?
አንዳንድ የታክሲ ባለንብረቶች ከአሽከርካሪዎች ጋር የሚገቡት ውል ተገቢ ያልሆነ ነው፡፡ ከአሽከርካሪ ጋር ውል ሲገቡ ሹፌሩ በሁሉም ነገር ተጠያቂነቱን መውሰድ አለበት፡፡ ታክሲ ስራ ሲያቆም ህዝቡ አገልግሎት ያጣል፤ ያን ጊዜ ባለቤቱ አሽከርካሪውን ለምን ብሎ መጠየቅና ታክሲው አገልግሎት እንዲሰጥ ካላደረገ ተጠያቂ ነው፡፡ በዚህ አግባብ ይመስለኛል የታክሲው ታርጋ የተፈታው፡፡ ውል ሲዋዋሉ ባለንብረቶች ሹፌሩን ሙሉ ተጠያቂ ካደረጉ እነሱ ነፃ ናቸው፡፡ ካልሆነ ግን ታክሲው ህዝብ ማገልገሉን ሲያቆም የማይጠየቁበት ምክንያት የለም፡፡
ህጉ ካልተሻሻለ አንሰራም ብለው በድጋሚ አድማ ቢመቱ ምን ታደርጋላችሁ?
እንዲህ አይነት አድማ ይደገማል ብለን አናስብም፤ አይደገምምም፡፡
በምን እርግጠኛ መሆን ይቻላል?
መቶ በመቶ እርግጠኛ መሆን አይቻልም፡፡ ሊከሰት ይችላል፡፡ መንግስት ግን በዋናነት እየሰራው ያለው ትልቅ ስራ አለ፤ ይህም ትራንስፖርቱን ከታክሲ ተፅዕኖ ማላቀቅ ነው፡፡ ወደፊት ታክሲ አማራጭ ትራንስፖርት እንጂ ዋና የትራንስፖርት አውታር መሆኑ ይቀራል፡፡
እንዴት ነው ትራንስፖርቱን ከታክሲ ተፅዕኖ ለማላቀቅ የታሰበው?
አንደኛው መንገድ የአንበሳ አውቶቡሶችን ቁጥር ማብዛት ነው፡፡ ሌላው የግል የአውቶብስ ድርጅቶችን ማበረታታት ነው፡፡ ለምሳሌ አሊያንስ ትራንስፖርት በስራ ላይ ያለ የትራንስፖርት ድርጅት ነው፡፡ በቅርቡ 300 አውቶብሶችን ጨምሮ ስራውን ይቀጥላል፡፡ መንግስትም በመጪው ግንቦትና ሰኔ ወር አካባቢ “ሸገር የብዙሀን አውቶቡስ ድርጅት” በሚል ድርጅት አማካኝነት 300 አውቶቡሶችን ይዞ ስራ ይጀምራል፡፡ ፐብሊክ አውቶቡሶችም በስፋት እየሰሩ ነው፡፡
አድማው በተከሰተ ጊዜ እነዚሁ ባሶችና አንበሳ አውቶቡስ የማህበረሰቡን የትራንስፖርት ችግር ለመፍታት ከፍተኛ ስራ ሲሰሩ ነበር፡፡ በእነዚህና መሰል አማራጮች ትራንስፖርቱን ከታክሲው ተፅዕኖ ለማውጣት ታስቧል፡፡

“ኢትዮጵያ ውስጥ የብዙኃን አስተሳሰብ ተጨፍልቋል”

ባለፉት 4 ወራት በኦሮሚያ ክልል የተፈጠረውን ተቃውሞና ግጭት እንዲሁም በተለያዩ የሀገሪቱ
አካባቢዎች የተከሰቱ ብጥብጦችን አስመልክቶ አንጋፋው ፖለቲከኛ አቶ ልደቱ አያሌው፤ከአዲስ አድማስ ጋዜጠኛ አለማየሁ አንበሴ ጋር በነበራቸው ቆይታ የሚከተለውን ትንታኔ ሰጥተዋል

   ዘንድሮ በሀገሪቱ የተለያዩ አካባቢዎች ለምን ተቃውሞና ግጭቶች የበዙ ይመስልዎታል?
የፖለቲካ እንቅስቃሴ ማድረግ ከጀመርን አንስቶ፣ ስርአቱ እንደ ስርአት ያለው አቅጣጫ ልዩነት ላይ የሚያተኩር ስለሆነ፣ በሂደት የህዝብን ትስስርና አብሮ የመኖር ሁኔታ እየሸረሸረ፣ ግጭቶችን እንደሚያባብስ ስንገልፅ ነበር፡፡ በአንፃሩ ኢህአዴግ የያዝኩት መንገድ ይበልጥ የህዝቡን አንድነት የሚያጠናክር ነው የሚል አቋም ላለፉት 25 አመታት ይዞ ቀጥሏል፡፡ ነገር ግን በእነዚህ ጊዜያት የሰላም ኮንፈረንስ ሲያካሂድ ነው የኖረው፡፡ ሰላም የሰፈነበት ሁኔታ አልታየም፡፡ አሁን ደግሞ በመጠኑም ሆነ በይዘቱ አቅጣጫውን የቀየረ አስቸጋሪ ሁኔታ በሀገሪቱ እየተፈጠረ መሆኑን እያየን ነው፡፡ ከአሁን በፊት ግጭት ብቅ ይላል፤ ብዙም ሳይታይ ይዳፈናል፡፡ ሌላ ጊዜ ደግሞ ብቅ ይላል፡፡ አሁን ግን ቀጣይ ግጭቶችና አለመግባባቶችን በብዙ አካባቢዎች እያየን ነው፡፡ ኢህአዴግ በአጠቃላይ በህዝቦች አንድነት ላይ ሳይሆን ለልዩነት ትኩረት ሰጥቶ የሚያራምደው ፕሮፓጋንዳ፣በሂደት ውጤቱ ምን እንደሆነ እየታየ ነው፡፡ ይሄ እንግዲህ በቀጥታ ከፌደራል ስርአት አደረጃጀቱ ጋር ይያያዛል፤ቋንቋና ብሄርን መሰረት አድርገው ከተደራጁ ፓርቲዎች አጠቃላይ ሁኔታም ጋር ይገናኛል፡፡
በአሁኑ ወቅት ችግሮቹ ለምን እየተባባሱ መጡ?
አንዱና ዋናው ጉዳይ ህብረተሰቡ በሰላማዊ መንገድ ሃሳቡን የሚገልፅበት እድል እየጠበበ መምጣቱ ነው፡፡ ስርአቱ በአንድ የፖለቲካ ፓርቲ የበላይነት ብቻ የሚመራ መሆኑና የህብረተሰቡ አስተሳሰብና ጥቅሞች የሚወከሉበት ም/ቤት ከቀበሌ ጀምሮ እስከ ፓርላማ መጥፋቱ ሌላው ነው፡፡ ኢህአዴግ ስለ ዲሞክራሲ ሲያወራ ትርጉም የሌለው የታይታ ዲሞክራሲ እንደሆነ፣ የተለያዩ ሃሳቦችም ተቀባይነት እንደሌላቸው ህብረተሰቡ እየተረዳ ነው የመጣው፡፡ ተቃዋሚ ፓርቲዎች ከቀበሌ እስከ ፓርላማ ም/ቤቶች ጥርግርግ ብለው መውጣታቸው ህዝቡ ብሶቱን የሚተነፍስበት መድረክ አሳጥቶታል። ህዝቡ መድረኩን ሲያጣ ሊከተል የሚችለው አማራጭ አመፅንና ተቃውሞን ነው፡፡
ቀደም ሲል ይሄ አልታየም፤ ምክንያቱም ቢያንስ በርከት ያሉ ፕሬሶች ነበሩ፡፡ ተቃዋሚዎች በፓርላማ ነበሩ፡፡ በፖለቲካ ፓርቲዎች መካከል ክርክሮች ይካሄዱ ነበር፡፡ ህዝባዊ ስብሰባዎችም ይደረጋሉ። በአጠቃላይ የተለያዩ የህብረተሰቡ ቅራኔዎችና ሃሳቦች የሚስተናገዱበት እድል ነበረ፡፡ በመሆኑም ህብረተሰቡ ወደ አመፅና ግጭት የመሄድ እድሉ እምብዛም ነበር፡፡ አሁን በሂደት ይሄ እየጠፋና መድረኩ እየጠበበ በመምጣቱና ፍፁማዊ የአንድ ፓርቲ የበላይነት በመንገሱ ለአመፅና ግጭቶች በር ከፍቷል፡፡ መንግስት ሰላማዊ ትግልንም ፈርቶ፣ የትጥቅ ትግልንም ፈርቶ መኖር አይችልም፡፡ አንዱን መምረጥ አለበት፡፡ የፖለቲካና የአመለካከት ልዩነት የሚስተናገድበት መድረክ ከሌለ፣ አመፅና የትጥቅ ትግል ምቹ መደላድል እያገኘ እንደሚሄድ መታወቅ አለበት፡፡ የተፈጠረው ችግርም የዚህ ሁሉ መግለጫ ነው፡፡
አመፅና ግጭቶቹ የመብት ጥያቄ ብቻ ሳይሆን የብሄር አክራሪነት የታከለባቸው ናቸው የሚሉ ወገኖች አሉ፡፡ የእርስዎ አስተያየት ምንድን ነው?
ህብረተሰቡ በታሪኩ አብሮ የኖረ ህብረተሰብ ነው፡፡ በልዩነት የመኖሩን ያህል ብዙ የአንድነት መገለጫ የሆኑ እሴቶች አሉት፡፡ ባለፉት 25 ዓመታት ግን ሲሰበክ የኖረው ልዩነቱ ነው እንጂ አንድነቱ አልነበረም፡፡ በዚህ ህብረተሰቡ “እኛና እነሱ” የሚል አመለካከት እንዲያዳብር ነው የተደረገው። ይሄ ሂደት ወደ ጠባብነትና ዘረኝነት የሚያመራ አደጋ እንደሚፈጥር ግልፅ ነው፡፡ አሁን እያየን ያለነው ይሄን ነው፡፡ አሁን እያየን ያለነው ሃገራዊ ራዕይ ሳይሆን አካባቢያዊ ሁኔታን ነው፡፡ እኛ ብሎ “እነሱ” የሚባሉትን የሚጠላ ኃይል ነው እየተፈጠረ ያለው፡፡ በኔ ሀብት ማንም ሊጠቀም አይገባም ብሎ የሚያምን ህብረተሰብ ነው እየተፈጠረ ያለው፡፡
ጤናማ ያልሆነ ጥላቻ የታከለበት ፉክክር ነው እየዳበረ የመጣው፡፡ ስርአቱምኮ የጠባብነት ችግር እንዳለበት ይናገራል፡፡ ግን ይሄን የጠባብነት አመለካከት ወደዚህ ደረጃ ያጎለበተው ማን ሆነና ነው ዛሬ እሱ ወቃሽ የሆነው? አሁን እያጨድን ያለነው የዚህን ፍሬ ነው፡፡፡ ይሄ ሀገር ወዴት እየሄደ ነው ተብሎ ተገምግሞ መሰረታዊ ማሻሻያ መወሰድ ካልተቻለ አደገኛ ነው፡፡ በተሃድሶ ላይ በር የዘጋ ስርአት አመፅና አብዮት ነው የሚያስተናግደው፣ ይሄ በታሪክ የተረጋገጠ ነው፡፡ ስለዚህ ኢህአዴግ ሰላማዊና ህጋዊ መንገዱን ባጠበበ ቁጥር ሊያስተናግድ የሚገደደው አመፅና አብዮት ነው፡፡
ኢህአዴግ ያለፈውን ምርጫ መቶ በመቶ አሸነፍኩ ሲል አደጋው ሊታየው ይገባ ነበር።  ኢትዮጵያ ውስጥ አሁን የብዙሃን አስተሳሰብ ተጨፍልቋል፡፡ አንድ አስተሳሰብ ብቻ የህብረተሰቡን ህይወት እየወሰነ ነው፡፡ በዚህ ሁኔታ የብዙሃን አስተሳሰብና ፓርቲ ስርአት አስፍነናል ማለት በህዝብ ላይ መቀለድ ነው፡፡ ኢህአዴግ በሌሎች ላይ ጣት መቀሰሩ የትም አያደርሰውም፤ ራሱን ነው መመርመር ያለበት፡፡ ተቀናቃኙም ሃይል ቢሆን አመፅና ግጭት ይህቺን ሀገር ወዴት ሊወስዳት እንደሚችል ቆም ብሎ ማሰብ አለበት፡፡ ህጋዊና ሰላማዊ መንገድ መከተል ያስፈልጋል፡፡ ምክንያቱም እንዲህ ያለው ብጥብጥ ኢትዮጵያን ወደ አልተፈለገ አቅጣጫ ሊወስዳት ይችላል፡፡
መንግስት ችግሩን እያስተናገደ ያለበት ሁኔታ ያዋጣል ብለው ያስባሉ?
እንግዲህ ችግሩን ከህብረተሰቡ ጋር እየተወያየሁ እየፈታሁ ነው ይላል፡፡ በኛ ግምገማ ግን መንግስት በቀጥታ ከጉዳዩ ባለቤት ጋር ሲወያይ አይደለም የምናየው፤ የራሱን ካድሬዎች እየሰበሰበ ነው እያወያየ ያለው፡፡ የራሱን ካድሬዎች ያወያያል፤ በቴሌቭዥንና በሬዲዮ ይቀረፃል፤ ያ ለህዝብ ይቀርባል፡፡ ይሄ መሬት ላይ ካለው እውነት ጋር አይሄድም፡፡ ህዝቡ የመንግስት ሚዲያዎችን በዚህ የተነሳ ማየት አይፈለግም፤ ሌሎች የውጭ አማራጮችን ይሻል። 25 ዓመት ሙሉ በሚዲያዎች እየተሰራ ያለው ፕሮፓጋንዳ፣ ስርአቱን በህዝብ ዘንድ አመኔታ እንዲያጣ አድርጎታል፡፡ ህዝብና መንግስትን ሆድና ጀርባ አድርጎታል፡፡ አሁን መንግስትን የሚያምን ህዝብ  የለም፡፡ በዚህ ምክንያት ነው አመፅና የትጥቅ እንቅስቃሴዎች ካለፈው ጊዜ በተሻለ እድል እያገኙ የመጡት፡፡
ባለፉት 4 ወራት በተከሰቱ ግጭቶች የበርካቶች ህይወት መጥፋቱ ተገልጿል፡፡ እልባቱ ምንድን ነው ብለው ያስባሉ?
በዚህ ጉዳይ ብዙ ድርድር ውስጥ መግባት አያስፈልግም፡፡ እነ ቱኒዚያ፣ ግብፅ፣ ሶርያ… አሁን ያሉበት ችግር ውስጥ የገቡት ተሃድሶ ማካሄድ አቅቷቸው ነው፡፡ ስርአቶቹ ቆም ብለው ራሳቸውን ገምግመው፣ ተሃድሶ ማድረግ አቅቷቸው ነው አብዮት ተቀስቅሶ ለራሳቸውም ለህዝባቸውም የማይጠቅም ሁኔታ ውስጥ የገቡት፡፡ የኢትዮጵያ መንግስትም ቆም ብሎ ተሃድሶ የማያደርግ ከሆነ፣ እነሱ የደረሰባቸው እጣ ፈንታ በሱም ላይ የማይደርስበት ምክንያት የለም፡፡ ችግሩ ግን በመንግስት ላይ ደርሶ የሚቆም አይደለም፡፡ ለሀገርና ለህዝብ የሚተርፍ ነው፡፡ በተለይ በሀገሪቱ ባለው የፖለቲካ ቅራኔና የልዩነት ስፋት እንዲሁም ሲሰብክ ከኖረው የጠባብነት አስተሳሰብ አንፃር፣ በግብፅና በሊቢያ የተፈጠረው አይነት እዚህ ቢያጋጥም፣ የሀገሪቱን ህልውና አደጋ ውስጥ የሚከት ነው የሚሆነው፡፡ ችግሩ ቢከሰት የአደጋው ተጠቂ የሚሆነው መንግስት ብቻ ነው ብሎ ማሰብ ተገቢ አይሆንም፡፡ መንግስት ይሄን አደጋ በሚገባ ተገንዝቦ ራሱን ለተሃድሶ ዝግጁ ማድረግ አለበት፡፡
ለተሃድሶ ዝግጁ መሆን አለበት ሲሉ ምን ማለት ነው?
ለዚህ ሀገር የታይታ ሳይሆን እውነተኛ ዲሞክራሲ እንዲመጣ ጥረት ማድረግ አለበት፡፡ የህብረተሰቡ የተለያዩ አመለካከቶች የሚወከሉበት መድረክ መፍጠር መቻል አለበት፣ ፓርቲዎች በነፃነት ተንቀሳቅሰው፣ ልዩነታቸውንና ሃሳባቸውን የሚያራምዱበት ሁኔታ መኖር ይገባዋል፡፡ በየ5 ዓመቱ የሚካሄዱ ምርጫዎችም ይሄን የህብረተሰቡን የሀሳብ ልዩነት የሚያስተናግዱ መሆን አለባቸው፤ ለታይታ ብቻ መሆን የለባቸውም፡፡ ግጭቱን በሃይል ለተወሰነ ጊዜ ማስቆም ይቻል ይሆናል፤ በዘላቂነት ግን ማስቆም አይቻልም፡፡ ዘላቂው መፍትሄ ከተፈለገ፣ ሃቀኛ የሆነ ተሃድሶ መምጣት አለበት፡፡
ሰሞኑን የታክሲ ሾፌሮች አዲሱን የመንገድ ደህንነት ደንብ በመቃወም የሥራ ማቆም አድማ አድርገው ነበር፡፡ አድማው ተገቢ ነው ይላሉ?
የታክሲ ሹፌሮች ህይወታቸው የተመሰረተበት ስራ ስለሆነ ህጉ ሊያመጣባቸው የሚችለው ችግር ሊያሳስባቸው ይችላል፡፡ ሲያሳስባቸው ተቃውሞአቸውን ማቅረብ መብታቸው ነው፡፡ ይህን ማንም ሰው መቃወም ያለበት አይመስለኝም፡፡ ተቃውሞአቸውን ያቀረቡት በሰላማዊ መንገድ ነው። ስራ ማቆም አንድ የሰላማዊ ተቃውሞ መንገድ ነው። ታክሲዎች ሲቆሙ ዞሮ ዞሮ ህብረተሰቡ ይጎዳል፡፡ ስለዚህ ሹፌሮችና መንግስት ተወያይተው መፍትሄ ማበጀት አለባቸው፡፡ ግን በአጠቃላይ በኦሮሚያም ሆነ በአማራ ክልል ወይም በሌሎች አካባቢዎች የሚነሱት ተቃውሞዎች መነሻ ምክንያቶች ይኑራቸው እንጂ ጥያቄዎቹ ብዙ ናቸው፡፡ በአፄ ኃይለ ሥላሴ ዘመን የተከሰተውም ይሄ ነው፡፡ አንዳንድ ጥያቄዎች መነሻ እንጂ ዋነኛ ጥያቄዎች አይደሉም። በኦሮሚያ ያለው የማስተር ፕላን ጥያቄ ብቻ ነው ብሎ የሚያስብ ካለ ተሳስቷል፤ስረ መሰረቱን በደንብ መመርመር ያስፈልጋል፡፡
ለነዚህ ሁሉ የሀገሪቱ ችግሮች ምንድነው መፍትሄው ይላሉ ትሄ ያበጁለታል?
ህዝብና መንግስት እየተራራቁ እንደሆነ መንግስት ተገንዝቦ፣ ህዝቡ በአግባቡ ብሶቱንና ተቃውሞውን የሚያሰማበት መድረክ መፍቀድ አለበት፡፡ በአጠቃላይ በሀገሪቱ የሚካሄዱ ምርጫዎች እድል የሚሰጡ መሆን አለባቸው፡፡ አንዱ መፍትሄ ሰላማዊና ህጋዊ መንገዱን ማስፋት ነው፡፡ የብዙሃን ፓርቲ አሰራር ሰፍኖ ልዩነት፣ ብሶት፣ ተቃውሞ… የሚደመጥበት መድረክ ያስፈልጋል፣ አሁን ግን ይሄ የለም፤ የአንድ ፓርቲ ብቸኛ የበላይነትና ቁጥጥር ያለበት ሀገር ነው፡፡
ሁለተኛው ህገ-መንግስታችንን መመርመር ያስፈልጋል፡፡ በተለይ የፌደራል አደረጃጀቱን በተመለከተ አደረጃጀቱ 25 ዓመት ውስጥ አንድነታችን እያጠናከረ መጣ ወይ? በህብረተሰቦች ዘንድ መተማመንን መፈቃቀርን ነው ወይ ያመጣው? የሚለውን መመርመር ያስፈልጋል፡፡ መሻሻል ካለበት መሻሻል አለበት፡፡ አሁን የሚደረገው ወታደራዊ እርምጃ ለጊዜው ችግሩን ሊያስታግሰው ይችላል ግን ያዳፍነዋል እንጂ አያጠፋውም፤መልሶ መፈንዳቱ አይቀርም፡፡


• 11 ዋና አከፋፋዮች ታስረዋል፤ የዋስትና ጥያቄያቸው በፍ/ቤት ተቀባይነት አላገኘም
• በርካታ ሺ ሰዎች በአባልነት ተመዝግበዋል መግቢያ 4ሺ ብር ይከፈላል
• ቲያንስ 700 ገፅ ደብዳቤ፣ የ15ሺህ ሰዎች የድጋፍ ፊርማ ለጠ/ሚ ቢሮ አስገብቻለሁ ብሏል

   የቻይናው ኩባንያ ቲያንስ፤ ሰፊ የምልመላ ዘመቻ በርካታ ሺ ሰዎችን ያስተሳሰረ መረብ መዘርጋት አለመዘርጋቱ አይደለም አከራካሪው ጉዳይ፡፡ የመረቡ አሰራርና አላማ ነው አወዛጋቢው ጥያቄ። የቪታሚንና የሚኒራል ክኒኖችን እንዲሁም ቅባቶችን እንደሚሸጥ የሚገልፀው ቲያንስ፤ ለዚህም “የኔትዎርክ ግብይት”ን እንደሚጠቀም ይናገራል፡፡
አቃቤ ህግ በበኩሉ፤ የድርጅቱ አላማ ሸቀጣሸቀጥን መሸጥ ሳይሆን፣ በዚሁ ሽፋን የአባልነት መመዝገቢያ ክፍያ መሰብሰብ እንደሆነ ይገልፃል፡፡ የተዘረጋው መረብም፣ በፒራሚድ ቅርጽ የተሸረበ ነው ብሏል - አቃቤ ህግ፡፡ ኩባንያው የፒራሚዱ የላይኛውን ጫፍ በመያዝ ይመለምላል፡፡ አስር ሰዎችን ቢመለምል የፒራሚዱ 2ኛ ደረጃ ረድፍ ተፈጠረ ማለት ነው፡፡ ተመልማዮቹ በተራቸው፤ እያንዳንዳቸው አስር አስር ሰው መልምለው በአባልነት እየመዘገቡ ለኩባንያው ያስተላልፋሉ፤ እነሱም ኮሚሽን ያገኛሉ፡፡ መቶ አዳዲስ አባላት ተፈጠሩ ማለት ነው - የፒራሚዱ ሶስተኛ ረድፍ፡፡ እነዚህም  የከፈሉትን 4ሺ ብር ለማካካስ አዳዲስ አባላትን መመልመል አለባቸው፡፡   
መቶዎቹ አባላት አስር አስር ሰዎችን ሲመለምሉ፣ ለራሳቸው ኮሚሽን ያገኛሉ፤ ከነሱ በላይ ላሉት ቀደምት መልማዮችም ክፍያ ይደረግላቸዋል፡፡ ከታች ደግሞ አራተኛ ረድፍ ተፈጥሯል - አንድ ሺ አባላትን ያሳለፈ፡፡
እነዚህም በተራቸው፤ ኮሚሽን ለማግኘት 10ሺ አዳዲስ አባላትን መመልመል ሊኖርባቸው ነው - ከታች አምስተኛ ረድፍ በመፍጠር፡፡ እነዚህም እንዲሁ፣ ለአባልነት የከፈሉት ገንዘብ ቀልጦ እንዳይቀር 100ሺ አባላትን መመልመል የግድ ይሆንባቸዋል፡፡ እነዚህም ከኪሳራ ሊድኑ የሚችሉት አንድ ሚሊዮን አባላትን መልምለው ክፍያ ከተቀበሉ ብቻ ነው፡፡
እነዚህ ግን ለምዝገባ የከፈሉት ገንዘብ ቀልጦ ይቀራል፤ አዲስ አበባ ውስጥ አዲስ አባል ሆኖ ሊመለመል የሚችል 10 ሚሊዮን ሰው የለም፡፡
ከፒራሚዱ የላይኛው ጫፍ ላይ ያለው አውራ፣ ከስሩ ያሉት አስር ሰዎች፣ ምናልባትም ቀጥለው ያሉት መቶ ሰዎች፣ ብዙ ገንዘብ ይሰበስባሉ፤ ከታች ያሉት መቶ ሰዎች፤ ብዙ ገንዘብ ይሰበስባሉ፤ ከታች ያሉት ብዙ ሺ ሰዎች ግን ገንዘባቸው የውሃ ሽታ ሆኖ ይቀራል፡፡ ቲያንስ እንዲህ አይነት በፒራሚድ ቅርጽ የተሸረበ ኔትዎርክ ይጠቀማል ይላል አቃቤ ህግ፡፡ የቲያንስ ሃላፊዎች ግን ያስተባብላሉ፡፡ ጥራት ያለውን ምርት ለመሸጥ የኔትዎርክ ግብይትን አከናውናለሁ በማለትም ይከራከራል፡፡  የኔትዎርክ ግብይትን የሚደግፍም ሆነ የሚከለክል ህግ ስለሌለ፣ የንግድ ፈቃድ የተሰረዘብኝ አላግባብ ነው ብሏል ድርጅቱ፡፡ ለጠቅላይ ሚኒስትር ጽ/ቤት 700 ገፅ ደብዳቤ፣ ከ15 ሺህ የድጋፍ ፊርማ ጋር አያይዤ አስገብቻለሁ ይላል፡
አቃቤ ህግ በበኩሉ፣ ቲያንስ በሸቀጥ ሽያጭ ሳይሆን በአዲስ አበባ አስር ክፍለ ከተሞች፣ የአባልነት ክፍያ እየጠየቀ ብዙ ገንዘብ ሰብስቧል ብሏል፡፡ በዚሁ መረብ አቀናባሪና አስፈፃሚ ሆነዋል ያላቸውን 11 ሰዎችንም ያሰረ ሲሆን፣ ተጠርጣሪዎች ከትናንት በስቲያ ፍ/ቤት ቀርበው በዋስ እንዲለቀቁ ጠይቀዋል፡፡ ይህን እንደሚቃወም የገለፀው አቃቤ ህግ፣ ምርመራ ለማጠናቀቅ ተጨማሪ ጊዜ ያስፈልገኛል ብሏል፡፡ ፍ/ቤቱ የሁለት ሳምንት ጊዜ በመፍቀዱ ተጠርጣሪዎቹ በእስር ይቆያሉ ተብሏል፡፡