Administrator

Administrator

Tuesday, 03 October 2023 00:00

ዝምተኛ ልቦች

አርቲስት ጌትነት እንየው
አምነው የወደዱ፣
ወደው የተካዱ፣
ተክደው የራዱ፣
ፍርሃት አንሸራቶ ቁልቁል የጣላቸው፣
የብቸኛ ልቦች የትነው መውደቂያቸው?
የትነው መድረካቸው?
ማነው አጃቢያቸው?
እንዴት ነው ምታቸው?
የተካዱ ልቦች አጋር የራቃቸው፣
የሚያቀነቅኑት ምንድን ነው ዜማቸው?
የተመረኮዙት እምነት ታጥፎባቸው፣
ድንገት የወደቁ ፍቅር ያዳጣቸው፣
ሚስጥር የሚያጋሩት ሰው የበረዳቸው፣
ብቸኝነት ሰርጎ ብቻ ያስቀራቸው፣
ዝምተኛ ልቦች ምን ይሆን ቋንቋቸው?
ከየት ነው ጥሪያቸው?
በየት ነው ጉዟቸው?
የት ነው መድረሻቸው?
እንደ ሰብአሰገል ጠቅሶ የሚመራቸው፣
የቃተቱ ልቦች የታል ኮከባቸው?
መቼም ከአምላክ ትንፋሽ ከውሃ ከአፈሩ፣
ከእምንት እና እውነት ከፍቅር ሲሰሩ፣
ዝምተኛ ልቦች ጥንቱን ሲፈጥሩ፣
ተገፍትረው ወድቀው፣
ደቀው እንዳይቀሩ፣
በተስፋ ጸንተው ነው ዘላለም ሊኖሩ።
አርቲስት ጌትነት እንየው ባለ ብዙ መልክ የጥበብ ስብእና ያለው ነው። ተውኔት ይፅፋል፣ ያዘጋጃል፣ ይተውናል። ግጥም ይፅፋል ።ደግሞም ደራሲ ነው። ለሃገራችን የኪነጥበብ ጉዞ ሁለገብ አስተዋፅኦ ከሚያበረክቱ የሀገራችን ከያኒዎች መካከል አንዱና ግንባር ቀደም ነው። ብዙዎች የቃላት ሃብት አለው ይሉታል። ቴአትርን ማዘመን ፤ ለቴአትር ህይወት መስጠትን ደግሞ ተክኖበታል። ታላቁ ባለቅኔ ጌትነት እንየው። የህይወት ታሪኩን እዝራ እጅጉ እና ዘቢባ ሁሴን ሰንደውታል፡፡
➻ ውልደት እና እድገት
ጌትነት እንየው ከጎጃም ምድር የፈለቀ ጠቢብ ነው። ወላጆቹ አርሶ አደሮች እርሱም የገበሬ ልጅ ነው። በደብረማርቆስ ከተማ አብማ ማርያም በምትባል መንደር በ 1950 ዓ.ም ተወልዷል።
ጌትነት ያደገው ከታላቅ እህቱ እና ከባለቤቷ ጋር ደብረማርቆስ ከተማ ሲሆን በ 1964 ዓ.ም የእህቱ ባል በስራ ምክንያት ወደ ጅማ ሲዘዋወር ጌትነትም ከእህቱና ከባለቤቷ ጋር ወደ አባጅፋር ሃገር ጂማ ተጓዘ።
የአንደኛ ደረጃ ትምህርቱን በጎጃም፣ ሁለተኛ ደረጃ ትምህርቱን ደግሞ በጅማ ተምሯል። ገና በለጋ እድሜው በመጀመሪያ ደረጃ ትምህርት ቤት ሳለ የተጠናወተው የኪነ-ጥበብ አባዜ በጅማም አብሮት ነበር።
➻ አዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ
ጌትነት ትምህርቱን አጠናቆም በጥሩ ውጤት ወደ ዩኒቨርሲቲ መግባት ችሏል። በ 1971 ዓ.ም የመጀመሪያ ምርጫው የሆነውን የትያትር ጥበብን ማጥናት ቀጠለ።
በዩኒቨርሲቲ ቆይታውም የግቢውን ባህል ማዕከል እንደርሱ በሚገባ የተጠቀመበት አልነበረም። ባህል ማዕከል ራሱን የሚፈትሽበት እና ራሱን የቀረፀበት ትወናን በማንያዘዋል እንዳሻው "በጠልፎ በኪሴ" ዝግጅት የጀመረበት የራሱንም የመጀመሪያ ተውኔት "ስንብትን" አዘጋጅቶ ለመድረክ ያበቃበት ባለውለታው ስፍራ ነበር።
ጌትነት በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ሲማር ዘወትር ኬኔዲ ላይብረሪ እየገባ በርካታ መፅሃፍትን ያነብ ነበር። አባኮስትር የተጠነሰሰው ያኔ ነው። አባኮስትር የካቲት መፅሄትን ሲያነብ ያገኘውና የተሳበበት ሀሳብን ያነሳበት ስራው ነበር።
ጌትነት ከአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ የትያትር ትምህርቱን በ 1974 ዓ.ም ተመርቆ ወጥቶ በ 1975 ዓ.ም ለተመረቁ ተማሪዎች የመመረቂያ እለት ስለ እናት ፣ ስለ ሃገር፣ ስለማገልገል የሚሰብክ መዝሙርን አዘጋጅቶ ነበር።
ትምህርቱን ካጠናቀቀ በኋላ ወዲያው በዝና እንጂ በውል በማያውቀው ብሄራዊ ትያትር ቤት ገብቶ ህልሙን እውን ማድረግ ጀመረ። በብሄራዊ ትያትር በነበረው ቆይታም ከተመልካች አእምሮ ውስጥ በጉልህ የተጻፉ ስራውን ማቅረብ ችሏል፡፡
ጌትነት ጎበዝ ገጣሚም ነው። ግጥምን የሚያነብበት መንገድ ከማንም ጋር የማይመሳሰል የራሱ ዜማ ያለው ፣ ወኔውና ስሜቱ ከነድምፀቱ እጅግ የሚማርክና የሚነዝር ነው።
➻ አበርክቶዎች
የኢትዮጵያ ኪነጥበብ ዋርካ !ታላቁ ከያኒ ፀሐፊ ተውኔት ጌትነት እንየው በቴአትር ድርሰት ፣ በዝግጅት ፣ በትወና እና በገጣሚነት ዘመን ተሻጋሪ የሆኑ በርካታ ጥንቅቅ ያሉ ስራዎችን ያበረከተ ፣ ሥነሥርዓት ሞልቶ የተረፈው ጨዋ ፣ ስራዎቹ በፍቅር የሚታዩለት ፣ የኪነጥበብ ታላቅ ሰው ነው። ከስራዎቹ ውስጥ ፦
➻ "ውበትን_ፍለጋ "
ይህ የጌትነት እንየው ድንቅ ተውኔት ሲሆን ግሩም አድርጎ ፅፎት ድንቅ አድርጎም አዘጋጅቶታል። ይኼ ቴአትር የመድረክ ዕይታው ሲጠናቀቅ ወደፊልም ተቀይሮም ተሰርቷል። ወደፊልም ሲቀየር ጌትነት እንየው የመሪ ተዋናዩን "ይገረሙ" የተሰኘውን ገፀ ባህሪ ወክሎ ተውኗል። ቴዎድሮስ ተስፋዬም ፊልሙን ዳይሬክት አድርጎለታል።
"ውበትን ፍለጋ" ጌትነት ከሰባት አመት በላይ የለፋበትና ውጤት ያገኘበት ተወዳጅ ተውኔት ነበር። የኔ የሚለው እምነትና ማንነቱም የተንፀባረቀበት ስራ ነበር። የአፃፃፍ ቴክኒኩ ከመምህሩ መንግስቱ ለማ ያገኘውን እውቀትም ተግባራዊ ያደረገበት ነው።
➻"በላይ_ዘለቀ" (አባኮስትር)
ይህን ቴአትር ጌትነት መድረክ ላይ ሲተውነው : በሚያስገመግም ድምፁ መድረኩ ላይ ጎብለል ጎብለል እያለ ሲምነሸነሽበትና ሲሞላው እጅግ ድንቅ ነው።
ጌትነት እንየው በላይ ዘለቀን ሲተውን ጥላሁን ገሰሰን በፍቅር ያንበረከከ በስራው ያሳመነ እና ያስጨበጨበ ሰው ነበር። ጥላሁን ገሰሰ ብቻ ሳይሆን በዘመኑ መድረክ ላይ የተመለከተው ሁሉ እጅግ የተደመመበት ታላቅ ስራ ነበር።
➻ " የእግዜር_ጣት"
ጌትነት እንየው የፃፈው ትያትር ሲሆን በዚህ ተውኔት ላይ ተስፋዬ ገ/ሃና ፣ አበባየሁ ታደሰ ፣ ስናፍቅሽ ተስፋዬ ፣ ህንፀተ ታደሰ እና ሱራፌል ወንድሙ ድንቅ ትወናቸውን አሳይተውበታል።
የድራማው ዋና ጭብጥ እግዚአብሔር ከፃፈው ውጪ ምንም ነገር ሊፈፀም አይችልም የሚል መልዕክት የሚያስተላልፍና ድንቅ አስተማሪ ቴአትር ነው።
➻"የቴዎድሮስ_ራዕይ"
ጌትነት ሙዚቃን ከትያትር ጋር አዋህዶ ታሪካዊና ሙዚቃዊ ተውኔቶችን መስራት ተክኖበታል። በዚህም "የቴዎድሮስ ራዕይ" ጉልህ ማሳያ ነው። ቴዎድሮስ ታሪካዊ ትያትር ሲሆን ከ 150 በላይ ተዋንያን የተሳተፉበት ስራ ነው።
ጌትነት ቴዎድሮስን የተመለከተው ሌሎች ካዩበት የሃይለኝነትና የጀግንነት ባህሪ በዘለለ ነው። የጌትነት "ቴዎድሮስ" እጅግ ለሰው የቀረበ ሰውነት ጎልቶ የሚታይበት አፍቃሪና ለፍቅር ተረቺነት ያለው ሰው ነው። ይህንንም ያሳየበት ድንቅ ስራ ነው።
ከበላይ ዘለቀ እና የቴዎድሮስ_ራዕይ ታሪካዊ ተውኔቶች በተጨማሪ "እቴጌ ጣይቱ" ቴአትርንም ፅፏል።
➻"ወይ_አዲስ_አበባ"
ይህ በ 1996 ዓ.ም የብሄራዊ ትያትር ቤት ለእድሳት ተዘግቶ ሲከፈት በአዲስ ስራ መከፈት አለበት ተብሎ በመታሰቡ በርካታ ተዋንያን የተሳተፉበት በጌትነት የተዘጋጀ ስራ ነው ።
ተውኔቱ የአፄ ሀይለስላሴን ፣ የደርግንና የኢህአዴግን የሶስቱንም መንግስታት የአገዛዝ ዘመን ቁልጭ አድርጎ የሚያሳይ ሙዚቃዊ ድራማ ሲሆን ጌትነት ፅፎና አዘጋጅቶ ከጨረሰ በኋላ ለዕይታ ሊበቃ በነበረበት ሰዓት በጊዜው መድረክ ላይ እንዳይታይ ቀጭን ትዕዛዝ ተላልፎ ታግዶበታል።
➻ ከላይ ከተዘረዘሩት በተጨማሪ ለእይታ የበቁ አጫጭርና የሙሉ ግዜ ተውኔቶች:-
1, ስንብት አአዩ የባህል ማዕከል 1974
2, የግርማ ቀላቢት በብሄራዊ ትያትር ቤት ለእይታ የቀረበ 1974
3, እንቁላል በብሄራዊ ትያትር ቤት እና በአሜሪካን ሀገር ለእይታ የቀረበ 1978-81
4, (final moment) እንግሊዘኛ ሲሆን ወደ አማርኛ ሲመለስ "እውነተኛ ቅፅበት " በብሄራዊ ትያትር ቤት: ካሜሮንና ስዊዲን ሃገር ለእይታ የቀረበ
5, ዲሞቴራፒ በብሄራዊ ትያትር ቤት ለእይታ የቀረበ 1985
6, ሃምሳ አመት ስንት ነው? በአ.አ ዩኒቨርሲቲ (50ኛ ዓመት ክብረ በዓል
= ጌትነት ከተወነባቸው ቴአትሮች መካከል፦
★ ባለካባ እና ባለዳባ ፣ አሉላ አባነጋ ፣ ነፃ ወንጀለኞች ፣የቬኑሱ ነጋዴ ፣ የእጮኛው ሚዜ ፣አንድ ጡት ፣ ውጫሌ አስራሰባት ፣ እርጉም ሀዋርያ እና ሐምሌት ከብዙዎቹ ጥቂቶቹ ናቸው።
= በዝግጅት ከተሳተፈባቸው ተውኔቶች ውስጥ፦
የለሊት እርግቦች ፣ የእግዜር ጣት ፣ ውበትን ፍለጋ ፣ ምስጢረኞቹ ፣ ሕንደኬ ፣የቴዎድሮስ ራዕይ ፣ አዙሪት ፣ አባትየው ( ትርጉም ተውኔት ) አዲስ ፀሐይ እና እቴጌ ጣይቱ ጀግና አዘጋጅ መሆኑን ያስመሰከረበት ስራዎቹ ሲሆኑ እነዚህንና ሌሎች ያልተካተቱ ቴአትሮች ላይ በመሪ ተዋናይነት በብቃት ተውኗል።
ጌትነት እንየው ከመድረክ ቲአትሮች በተጨማሪ ብዛት ያላቸው አጫጭር ልብ ወለዶችን፣ አጫጭር የሬዲዮና የቴሌቪዥን ሥራዎችን ለህዝብ አበርክቷል፣
★ “ላይመለስ”፣ “ዲሞቴራፒ”፣ “የቅርብ ሩቅ” እና ለ13 ተከታታይ ሳምንታት የቀረበው፣ “ጥንዶቹ” የተሰኙ የሬዲዮ ድራማዎች በብዙኃን የሬዲዮ ተደራሲያን ዘንድ እንዲታወቅ አድርጎታል::
ከእነዚህ ውስጥ “ላይመለስ” እና “የቅርብ ሩቅ” በሚል ርዕስ የሚታወቁት ድራማዎች በአገራችን ተከስቶ በነበረው ረሀብ ላይ የሚያጠነጥኑ ሥራዎች ሲሆኑ፣ በተለይ “ላይመለስ” የሚለው ሥራ በሬዲዮ ከመቅረቡ በፊት በቴሌቪዥን መታየቱ ይታወሳል፡፡
ጌትነት በሬዲዮ የመጻሕፍት ዓለም ፕሮግራም ላይ የሰርቅ ዳንኤልን፣ “ቆንጆዎቹ”ን ረዥም ልብወለድ መጽሐፍ መተረኩም ይታወቃል፡፡ የአተራረክ ስልቱ እጅግ በጣም ማራኪ በመሆኑ በጊዜው ከፍተኛ እውቅናን አስገኝቶለት ነበር፡፡ በርካታ የሙዚቃ ግጥሞችን ለሙዚቀኞች እንካችሁም ብሏል።
ጌትነት ለሀገሩ ያለው ፍቅር ልዩ ነው፡፡ በጥበባቸው ለህዝብ ከሚደርሱ ተዋንያን መካከል አንዱ ነው። ኢትዮጵያን በብእሩ አሞካሽቷታል። በነጎድጎዳማ ድምፁ አነብንቦላታል። በወኔ ገልጿታል። ለብዙ ችግሮቻችን መፍትሄ ብሎ በግጥሞቹ ተንፍሶልናል። አስቆናል። ደግሞም አስለቅሶናል።
➻ ምስጋናና ሽልማት
ጸሐፌ- ተውኔት፣ ገጣሚ፣ ተዋናይ እና አዘጋጅ ጌትነት እንየው ለጥበብ ላበረከተው አስተዋጽዖ በርካታ የእውቅና ምስጋናን ተችሮበታል፡ የአማራ ክልል ባህልና ኪነ-ጥበብ ፌስቲቫል "ለባህልና ኪነ-ጥበብ እድገት" ላበረከተው የላቀ አስተዋጽኦ የሕይወት ዘመን ተሸላሚ ሆኖ የክብር የእውቅና ሽልማት ሰጥቷታል።
በ 1991 ዓ.ም የኢትዮጵያ ሥነ ጥበባትና የመገናኛ ብዙኃን የሽልማት ድርጅት በቲአትር የረዥም ጊዜ አገልግሎት ተሸላሚም ነበር።
ጌትነት ከቲአትር ሙያ ጋር በተያያዘ ከኢትዮጵያ ውጪ ወደ ተለያዩ የዓለም ሃገራት የተዟዟረ ሲሆን፣ ከአፍሪካ ኬንያና ካሜሮን፣ ከአውሮፓ ስዊድንን፣ ከአሜሪካ የተለያዩ ስቴቶችን ጎብኝቷል፡፡ ወደ ቻይናም አቅንቶ የቲአትር ስልጠና ወስዶ ተመልሷል።
መዝጊያ፤ ይህ መዝጊያ የተወዳጅ ሚድያ እና ኮሚኒኬሽን አቋም የሚንጸባረቅበት ነው፡፡
ጌትነት እንየው ዛሬም የሙያ ክብሩን እንደጠበቀ ያለ ግሩም የኪነጥበብ ሰው ነው፡፡ በትወና ክህሎቱ ፤ በድርሰት እና በዝግጅት ብቃቱ ብዙ ባለሙያዎች መስክረውለታል፡፡ ስለ 1970ዎቹ አጋማሽ የሀገራችን የቴአትር ታሪክ ስናወሳ ጌትነት በዛን ዘመን ብቅ ካሉት አንዱ ነው፡፡ ጌትነት ከ 1975 ጀምሮ ላለፉት 40 አመታት በጽናት ሙያው ላይ የቆየ ነው፡፡ ለዚህ ጽናቱ ልናመሰግነው ግድ ይላል፡፡ የህይወት ታሪኩንም በዚህ መልኩ የሰነድነው የጽናት ተምሳሌትነቱን ለማሳየት ነው፡፡ ስለ ጌትነት ታዳሚያንም ልዩ ፍቅር እንዳላቸው አስተውለናል፡፡ በተለይ የቴዎድሮስ ራእይ ላይ ሲተውን ሙሉ ብቃቱን አሳይቷል፡፡ ታዲያ ጌትነት ከትወና እና ከዝግጅት ባሻገር ጎበዝ ገጣሚነቱም ተመስክሮለታል፡፡ እኛም ለአዲሱ ትውልድ አርአያ የሚሆን ስንል ታሪኩን ሰንደናል፡፡
ታሪክን_ወደኋላ
Tewedaji Media
የቴሌግራም ቻናልችንን በመቀላቀል የአዲስ አድማስን መረጃ ይከታተሉ…
 
Tuesday, 24 October 2023 00:00

የሎሚ ጥቅም

ሎሚ በዓለም ላይ በጣም ተወዳጅ ከሆኑ  የፍራፍሬ አይነቶች አንዱ ነው። ምንም እንደኳን ሎሚ ጣዕሙ ኮምጣጣ ቢሆንም በርካታ የጤና ጥቅሞች እንዳሉት የጤና ባለሙያዎች ያስረዳሉ፡፡
ሎሚ ለጤና ከሚያበረክታቸው ጥቅሞች መካከል የሚከተሉት ይገኙበታል፡፡

1: ሎሚ ለልብ ጤናን ያገለግላል፤

ሎሚ ጥሩ የቫይታሚን ሲ እና አንቲኦክሲደንትስ ምንጭ መሆኑን ጥናቶች ያመለክታሉ፡፡ እነዚህ  ንጥረ ነገሮች ለልብ ጤንነት ጠቃሚ ከመሆናቸውም በላይ ለልብ ህመም እና ስትሮክን ለመከላከል የሚያገለግሉ ሲሆን በሎሚ ውስጥ የሚገኙ አንዳንድ ፋይበሮች ደግሞ ለልብ ሕመም የሚያጋልጡ ሁኔታዎችን በእጅጉ ሊቀንሱ እንደሚችሉ የጤና መረጃዎች ያመላክታሉ፡፡
የሎሚ ጭማቂ መውሰድ የደም ግፊትን ለመቀነስ እንደሚረዳ ጥናቶች አረጋግጠዋል።

2. ሎሚ በሽታ የመከላከል አቅምን ከፍ ያደርጋል፤

ሎሚ በሽታ የመከላከል አቅምን ከፍ የሚያደርግ ፍራፍሬ  በመሆኑ ለጉንፋን እና ለጉንፋን መሰል በሽታዎች  መንስኤ የሚሆኑ ጀርሞችን የመከላከል አቅምን ይገነባል። አንድ ብርጭቆ የሞቀ ውሃ በሎሚ ጭማቂ በአንድ የሾርባ ማንኪያ መውሰድ ሳልንና ጉንፋን ለመከላከል እንደሚያግዝ የጤና ባለሙያዎች ይመክራሉ፡፡

3: ሎሚ ለምግብ መፈጨት የጎላ አስተዋጽኦ አለው፤

ሎሚ ከፍተኛ መጠን ያለው የሚሟሟ ፋይበር የያዘ በመሆኑ መደበኛ የአንጀት እንቅስቃሴን ለመጠበቅ እና የምግብ መፈጨትን እንደሚያሻሽል የጤና መረጃዎች ያመላከታሉ። በሎሚ ውስጥ የሚገኘው ፖክቲን የተባለው ፋይበር የስታርች እና የስኳር የምግብ አይነቶችን በመፈጨትና በማፋጠን  የአንጀት ጤናን ለማሻሻል ይረዳል።

4.  ሎሚ  ክብደትን ለመቆጣጠር ያግዛል፤

ሙሉ በሙሉ የተጨመቀ ሎሚ በአንድ ብርጭቆ ለብ ባለ ውሃ አንድ የሾርባ ማንኪያ ማር በማድረገ መጠጣት ክብደትን ለመቀነስ እንደሚረዳ የጤና መረጃዎች ያስረዳሉ። ሎሚ  ክብደትን የሚጨምሩ ጤናማ ያልሆኑ ምግቦችን ከመመገብ የሚከለከል  ፔክቲን የተባለ ንጥረ ነገር ያለው በመሆኑ ለክብደት መቀነስ ጠቀሜታው የጎላ ነው፡፡
አንዳንድ ጥናቶች እንደሚያመለክቱት በሎሚ ውስጥ የሚገኙት አንቲኦክሲደንትስ ክብደትን ለመቆጣጠር ይጠቅማሉ፡፡

5፡ ሎሚ የካንሰር ተጋላጭነትን ለመቀነስ ይረዳል፤

ሎሚ እና የሎሚ ጭማቂ የበለፀጉ የቫይታሚን ሲ ምንጭ በመሆናቸው እንደ ካንሰር ያሉ ገዳይ በሽታዎችን ለመከላከል የሚረዱ ፀረ-አንቲኦክሲዳንቶች እንዳሏቸው የጤና መረጃዎች ያመልክታሉ፡፡

6: ሎሚ በአፍ ውስጥ የሚከሰትን ህመም ያስታግሳል፤

ቫይታሚን ሲ ለጥርስ እና ለድድ አስፈላጊ በመሆኑና ሎሚ ደግሞ  በቫይታሚን ሲ የበለፀገ በመሆኑ በአፍ ውስጥ የሚከሰቱ በሽታዎች ለመከላከል ይጠቅማል። ስኩዊቪ በቫይታሚን ሲ እጥረት የሚመጣ በሽታ ሲሆን  ለድድ እብጠት፣ መድማት ወዘተ የሚዳርግ በሽታ ሲሆን ሎሚን በመጠቀም ይህን በሽታ ለመከላከል ያግዛል እንደ ጤና ባለሙያዎች መረጃ፡፡

7: ሎሚ ለቆዳ ጠቃሚ፤

ሎሚ ከፍተኛ መጠን ያለው የቫይታሚን ሲ ይዘት ስላለው ለቆዳችን ወፍራም እና ወጣት መልክ የሚሰጠውን ኮላጅንን ያመነጫል፡፡ ኮላችን ቆዳችንን እንዲያመር ከማድረጉም ባለፈ በፊት ላይ የሚገኙ ጥቃቅን መስመሮችን ለመቀነስ እና ቆዳን ለማጥራት ያገለግላል፡፡

ሎሚ በረካታ  ንጥረ ነገሮች ያሉት በመሆኑ ከተለያዩ  ምግቦች ጋር መጠቀም መቻል የበለጠ ገንቢ እና ጤናማ ቆዳ እንዲኖር ያደርጋል፡፡

የሎሚ ዘይት ጭንቀትን በማረጋጋት እና መንፈስን በማደስ ስሜትን ሊያሻሽል እንደሚችልም ነው የጤና ባለሙያዎች የሚያስረዱት።

8. ሎሚ የኩላሊት ጠጠርን ለመከላከል ይረዳል፤

በትኩስ ፍራፍሬ ውስጥ የሚገኘው ከፍተኛ የሲትሪክ አሲድ እና የሎሚ ጭማቂ ክምችት የሽንት መጠንን ሳይቀይር የሽንት ሲትሬትን መጠን በሁለት እጥፍ ለማሻሻል ያስችላል፡፡ ጥናቶች እንደሚያሳዩት የሎሚ ጭማቂ የኩላሊት ጠጠርን ለመከላከል የሽንት ሲትሬትን በመፍጠር ለክሪስታል እድገት መከላከያ ዘዴ ሆኖ ተገኝቷል፡፡

9. ሎሚ ለጉሮሮ ኢንፌክሽን ጠቃሚ፤

ሰዎች ጉሮሯቸውን በሚታመምበት ጊዜ  ብዙውን ጊዜ የሎሚ ጠብታዎችን እንዲጠቀሙ እንደሚመከር የጤና መረጃዎች ያመላክታሉ፡፡ምክንያቱም ሎሚ በተፈጥሮ ፀረ-ባክቴሪያ ባህሪያት ስላለው የባክቴሪያውን ተፅእኖ ስለሚቀንስ ነው፡፡

በአጠቃላይ ሎሚ በርካታ የጤና በረከቶች እንዳሉት በጤና ባለሙያዎች ይነገራል፡፡ስለዚህ ሎሚን የምግባችን አካል በማድረግ ጤናችንን መጠበቅ ይገባል፡፡

አንጋፋው ተመራማሪ ፕሮፌሰር ጋቢሳ ኢጄታ የአሜሪካን ብሄራዊ የሳይንስ ሜዳሊያ ሽልማትን ከፕሬዚደንት ጆ ባይደን ተቀብለዋል።
ፕሮፌሰር ጋቢሳ በፕሬዚዳንት ጆ ባይደን ብሔራዊ የክብር ሽልማት ከተሸለሙ 21 አሜሪካውያን ተመራማሪዎች መካከል አንዱ ሆነዋል።
መምህርና ተመራማሪው ፕሮፌሰር ጋቢሳ ኤጄታ ለሽልማቱ ያበቃቸው በከፍተኛ የምርምር ስራቸው የእፅዋት ዘረመል ምህንድስና በመጠቀም በረሃማ የአየር ንብረት እና ነፍሳትን የሚቋቋሙ የአዝርዕት ዘሮችን በማግኘታቸው ነው።
ግኝታቸው በሚሊዮን ለሚቆጠሩ የምግብ ዋስትናን እንደሚያረጋግጥ ታምኖበታል።
ፕሮፌሰር ጋቢሳ ኤጄታ በምግብ ዘርፍ ላበረከቱት አስተዋፅዖ ከዚህ በፊት ከዓለም የምግብ ፕሮግራሙ ሽልማት የተበረከተላቸው መሆኑ የሚታወቅ ነው።
ፕሬዚደንት ባይደን በይፋዊ የማህበራዊ ትስስር ገፃቸው ይፋ ባድረጉት የተሸላሚዎች ዝርዝር በሳይንስ፣ ቴክኖሎጂና ፈጠራ ዘርፍ ለሽልማት የበቁትን ተመራማሪዎች እንኳን ደስ ያላችሁ ብለዋል።
ከንቲባ ዶ/ር አዳነች አቤቤ ለሕዝብ ተጠቃሚነት እና ለሰላም ላበረከቱት ታላቅ አስተዋፅዖ ፣ ያሳዩት በሳል እና ምሳሌያዊ አመራር በዓለም አቀፍ ደረጃ ለሚገኙ መሪዎች ምሳሌ የሚሆንና መነሳሳት የሚፈጥር በመሆኑ ዩኒቨርሲቲው ይህንን Doctorate of Philosophy እንዳበረከተላቸው የትሪኒቲ ኢንተርናሽናል አምባሳደሪስ ዩኒቨርሲቲ ቻንስለር ዶ/ር ዣክሊን ሞሀየር ገልፀዋል::
በዝቅተኛ የኑሮ ደረጃ ላይ የሚገኙ ነዋሪዎችን ህይወት ለመቀየር እና የነዋሪዎችን ፍትሃዊ ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ ከንቲባ ዶ/ር አዳነች አቤቤ ላሳዩት ቁርጠኝነት እና ለሌሎች ሃገራት መሪዎች አርአያ የሚሆን ስራ በመስራታቸው የጆርጂያ ግዛት የክብር ዜግነት ሽልማት እንደተበረከተላቸው የግዛቱ ሴናተር ጋይል ዴቨንፓርት በመድረኩ ላይ ተናግረዋል::
በመድረኩ ላይ ንግግር ያደረጉት ከንቲባ ዶ/ር አዳነች አቤቤ ለዚህ ስኬት የበኩላቸውን አስተዋፅዖ ላበረከቱ አካላት በሙሉ ምስጋናቸውን አቅርበዋል::
AAU Confers full professorships on seven faculty members.
1. ፕሮፌሰር ዮናስ ጨቡዴ
በኢንኦርጋኒከ ኮሚስተሪ
2. ፕሮፌሰር አህመድ ሙስጠፋ
በኮምፒቲሽናል ኬሚስተሪ
3. ፐሮፈሰር ኑርልኝ ተፈራ
በኬሚካል ኢነጂነሪንግ
4. ፐሮፌሰር አምቢሳ ቀነዓ
በጄነራል ኢዱኬሽን
5. ፕሮፌሰር ፈቃዱ ጋሻው
በፊዚክስ
6. ፐሮፌሰር አበባው ይረጋ
በሀየር ኢዱኬሽን
7. ፕሮፈሰር ታደሰ በሪሶ
በአንትሮፖሎጂ
Tuesday, 24 October 2023 19:53

https://online.fliphtml5.com/etocz/wusy/

* ወላጆችን በተደጋጋሚ ሀኪምን እንዲጎበኙ ምክኒያት ከሆኑ  ህመሞች አንዱ በተለምዶ ቁርጠት (Infantile colic) የሚባለው ነው። ቁርጠት በተወለዱ በመጀመሪው ወር በጨቅላ ህጻናት ላይ የሚከሰት ሲሆን በቀን ለሶስት ሰአትና ከዛ በላይ ፣ በሳምንት ለሶስት ቀናትና ከዛ በላይ እንዲሁም  ለሶስት ሳምንታትና ከዛ በላይ የሚቆይ የለቅሶና መነጫነጭ ስሜት ነው።  ስለዚሁ ህመም ወላጆች ማወቅ ያሉባቸው 10 ነጥቦችን በዛሬው ጽሁፍ ይዤ ቀርቤያለሁ እስከመጨረሻው አንብቡት።

1. የህፃናት ቁርጠት (infantile colic)  መንስኤው ምንድን ነው?

* በመንስኤው ላይ በህክምና ባለሙያዎች ዘንድ ወጥ የሆነ መግባባት ባይኖርም የአንጀትና ባጠቃላይ የስርአተ ልመት ኢንዛይሞች ከአለመጎልመስ ጋር የተያያዘ ነው ተብሎ ይታሰባል።

2. ህመሙ እስከ መቼ ይቀጥላል ?

* በአብዛኛው ህጻናት ዘንድ ህመሙ እስከ ሶስት ወር የሚቆይ ሲሆን  አልፎ አልፎ ግን በጣም ጥቂት ህጻናት ላይ እስከ ዘጠኝ ወር ሊዘልቅ ይችላል።

3. የምታጠባ እናት ከምትበላው ምግብ ጋር የቁርጠት ህመም ምን ግንኙነት አለው?

* የምታጠባ እናት  ቡና፣ ቅመም የበዛባቸው ምግቦች ወይም የላም ወተት ብትቀንስ ቁርጠት ላለባቸው ህፃናትን ቁርጠቱ እንዲቀንስላቸው ሊያግዝ ይችላል።

4. የጣሳ ወተትን በመቀየር ቁርጠትን መከላከል ይቻላል?

* ህጻኑ የጣሳ ወተት ሲወስድ የመነጫነጭና ማልቀስ ምልክት ካለው የጣሳ ወተቱን ቢቀየር ይመከራል ።

5. ቁርጠት ላለበት ልጅ መድሀኒት ቢሰጠው ለህመሙ ይረዳዋል?

* የቁርጠት መንስኤ የተለያዩ ምክኒያቶች በመሆናቸው እንዲሁም የህመሙ ባህሪ ከልጅ ልጅ ስለሚለያይ ለቁርጠት ወጥ የሆነ ህክምና የለውም። የተለያዩ ጥናቶች እንደሚያሳዩት መድሀኒት መስጠት ለቁርጠት ብዙ ጠቀሜታ አይሰጥም።

6. በወላጆች በኩል ቁርጠቱን ለማስታገስ ምን ቢደረግ ይመከራል?

* ህጻኑን ዘና እንዲልና እንዲረጋጋ የሚያደርጉ ለምሳሌ ገላን በሙቅ ውሀ ማጠብ፣ ለስለስ ባለ ብርድ ልብስ መጠቅለና፣ ጥንቃቄ በተሞላበት መልኩ ህጻኑን መወዝወዝ( rocking motion)፣ ለስላሳ ሙዚቃ መክፈትና እሹሹ እያሉ ማረጋጋት ህጻኑ ህመሙ ቀለል እንዲልለት ይረዳል።

7.  ለረጅም ሰአት ህጻኑ በማልቀሱ ምን ጉዳት ያመጣበታል?
* ህፃኑ ለረጅም ሰአት በማልቀሱ የሚመጣ ጉዳት የለም። ህጻኑ የአካል ጥንካሬው ጥሩ ከሆነ፣ በደምብ የሚጠባ እንዲሁም በጥሩ የእድገት ደረጃ ላይ ካለና ቆዳ ከለሩም ካልተለወጠ፣ የ ትኩሳት ምልክት ካልታየበት ከሰላሳ ደቂቃ በላይ ቢያለቅስም ያን ያህል አሳሳቢ አይደለም። ስለዚህ ወላጆች ህፃናትን ለማረጋጋት ከሚጠቀሙበት መንገዶች ውጪ ከ አምስት እስከ አስር ደቂቃ ህፃኑ እንዲያለቅሱ በመተው ራሱን በራሱ እንዲያረጋጋ ማድረግ ይቻላል ።

8. ቁርጠቱ ከሌላ ህመመ ጋር አለመያያዙን በምን ምርመራ ማወቅ ይቻላል?

* ለቁርጠት የሚደረግ ምርመራ የለም። ነገር ግን ቁርጠቱ ሲከሰት ህፃኑ በ ህፃናት ህክምና ባለሙያ እንዲታይ በማድረግ የችግሩ መንስኤ ቁርጠት ወይም ሌላ ህመም መሆኑን ማወቅ ይቻላል። ህጻኑ በህጻናት ህክምና ስፔሻሊስት   ከታየ በኋላ ከአንጀት ጋር የሚያያዝ ችግርን ከተጠረጠረ ራጅ ወይም አልትራሳውንድ ምርመራ እንደሁኔታው ሊታዘዝ ይችላል።

9. ቁርጠት የያዘውን ህፃን በሀኪም እንዲታይ ማድረግ ያለብን መቼ ነው?

* አብዛኞቹ የቁርጠት ህመሞች በተደጋጋሚ ጊዜ ሰአት ለይተው የሚከሰቱ ናቸው። ለምሳሌ ቁርጠቱ ማታ ማታ በተደጋጋሚ ሊከሰት ይችላል። ነገር ግን ለቅሶው ከተለመደው በጣም ከረዘመና ከህፃኑ ባህሪ ጋር ባልተለመደ መልኩ የሚከሰት ከሆነ ለሀኪም ማሳየቱ ይመከራል። ከዚህ በተጨማሪ የንቃት መቀነስ፣ ትኩሳት፣ ጡት አለመጥባት ወይም ምግብ ፍላጎት መቀነስ ፣ ተደጋጋሚ ትውከት፣ ያልተለመደ የሆድ ድርቀት ወይም ተቅማጥ፣ እና በፊንጢጣ የሚወጣ ደም ካለ ቶሎ ለሀኪም ማሳየት ያስፈልጋል።

10. ልጁ ቁርጠት እንዳለበት ከታወቀ ለክትትል መቼ መምጣት አለበት?

* አንድ ህፃን ቁርጠቱ ከሶስት ወይም ከአራት ወር በኋላ ከቀጠለ በሀኪም መታየት ይኖርበታል። 
በዶ/ር ኤርሚያስ አበባው ሲኒየር የህፃናት ህክምና ስፔሻሊስትና የማህበረሰብ ጤና ባለሙያ)

ዓለም አቀፍ የስታርትአፕ ሽልማት በአዲስ አበባ ይካሄዳል

ዓለም አቀፍ የስታርትአፕ ሽልማት ጉባዔ በአዲስ አበባ በሳይንስ ሙዚየም ከጥቅምት 14-16/2016 ይካሄዳል።
በጉባዔው ከ300 በላይ አህጉርና አለም አቀፍ የቴክኖሎጂ ፈጠራ ባለቤቶች ይወዳደራሉ።
ጉባዔውን አስመልክተው የስራና ክህሎት ሚኒስትር ወይዘሮ ሙፈሪያት ካሚል ለመገናኛ ብዙሃን መግለጫ ሰጥተዋል።
ሚኒስትሯ በመግለጫቸው ጉባዔው ከጥቅምት 14-16/ 2016 በሳይንስ ሙዚየም ይካሄዳል ብለዋል።
ከእነዚህ ውስጥ የተሻለ ስራ ይዘው ለቀረቡ 15 ተወዳዳሪዎች ሽልማት እንደሚበረከትም ተናግረዋል።
ጉባዔው የልምድ ልውውጥ የሚደረግበትና አለም አቀፍ ትስስር የሚፈጠርበት እንደሚሆንም አንስተዋል።
የኢትዮጵያን ትክክለኛ ገጽታ ለሌላው አለም በማስተዋወቅ ወደ አህጉርና አለም አቀፍ የቴክኖሎጂ ገበያ ለመግባት ይረዳልም ብለዋል።
ሚኒስትሯ አክለውም "ኔክስት ኢትዮጵያን ስታርትአፕ ኢኒሼቲቭ" ጥቅምት 13 ቀን 2016 ዓ.ም በአዲስ አበባ እንደሚካሄድ ተናግረዋል።
ይህም ለቴክኖሎጂ ልማት ምቹ ሁኔታ ለመፍጠር ጠቀሜታው የጎላ መሆኑን አመላክተዋል።
መድረኩ በስራና ክህሎት ሚኒስቴር እና በኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ሚኒስቴር ትብብር እንደሚዘጋጅ መገለጹን ኢዜአ ዘግቧል፡፡

Page 10 of 678