Administrator

Administrator

ባለ አራት ኮከቡ ዘጠነኛው ኃይሌ ሆቴል ወላይታ በዛሬው ዕለት አገልግሎት መስጠት መጀመሩን አብስሯል፡፡ ሆቴሉ  ትልቁን ዳሞታ ተራራን ተንተርሶ  በኮረብታማዋ ወላይታ ሶዶ ከተማ እምብርት ላይ የተገነባ ነው።

 ሆቴሉ ተሰርቶ ለመጠናቀቅ አራት ዓመታትን የፈጀ ሲሆን፤ እስካሁን 1 ነጥብ 1 ቢሊዮን ብር ወጥቶበታል ብሏል፤ በሆቴሉ ዳሞታ አዳራሽ ጋዜጣዊ መግለጫ የሰጠው ሻለቃ አትሌት ኃይሌ ገብረስላሴ።

 ሆቴሉ 107 ዘመናዊ የማረፊያ አልጋዎች፣ ከ15-600 ሰው የመያዝ አቅም ያላቸው 7 የስብሰባ አዳራሾች፣  የጤናና የውበት መጠበቂያ -  የጂም የሳውና የስቲም ባዝና የማሳጅ አገልግሎት  እንዲሁም የወላይታ ህዝብ የምግብ ሜኑን ጨምሮ የተለያዩ የሐገር ውስጥና ዓለም አቀፍ ምግቦችን የያዙ ሦስት ዘመናዊ ሬስቶራንቶች የለስላሳና የአልኮል መጠጦች አገልግሎት የሚሰጡ ሁለት ባሮችን በውስጡ ይዟል።

በአሁኑ ወቅት ለ160 ሰዎች የስራ እድል የፈጠረ ሲሆን፤ በሙሉ አቅሙ ስራ ሲጀምር ለ300 ሰዎች ቋሚ የስራ እድል እንደሚፈጥር ተገልጿል።

  "አንድ ኢንቨስተር  ኢንቨስት ሊያደርግ ሲነሳ መጀመሪያ የሚያየው የአካባቢው ህዝብና መንግስት ምን ያህል ቀና ናቸው የሚለውን ነው" ያለው ሐይሌ፤ የወላይታ ህዝብ ላሳየው ቅንነትና ትብብር አመስግኗል። ሆቴሉ የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ዋና መቀመጫ ለሆነችውና በፈጣን  እድገት ላይ ለምትገኘው ወላይታ ሶዶ ከተማም ሆነ ለነዋሪዎቿ ድምቀት  ብሎም የስራ እድል ይዞ የመጣ የህዝብ ሐብት ነው  ያለው ሐይሌ፤ ለቱሪዝም ፍሰትና ለኢኮኖሚ እንቅስቃሴ ጉልህ ሚና ይጫወታልም ብሏል።

ከ14 ዓመት በፊት በሐዋሳ ከተማ የተጀመረው የሐይሌ ሪዞርት፣ ዛሬ ላይ በተመሳሳይ የአገልግሎት ጥራት 9ኛ ሆቴሉን በወላይታ እያስመረቀ ሲሆን፤ በቀጣይ በጅማ በደብረ ብርሃንና በሻሸመኔ ሐይሌ ሆቴሎችና ሪዞርቶች ተከፍተው ስራ ይጀምራሉ ተብሏል።

 ኃይሌ በአካባቢው በተፈጠረ አለመረጋጋት የሻሸመኔና  በዝዋይ ያሉት ሆቴሎቹ ውድመት እንዳሳዘነው ገልፆ፣ ምንም እንኳን መንግስት  ካሳ ባይከፍለውም (እንዲከፍለኝ እጠብቃለሁ ብሏል)፤ሆቴሎቹ ግን መገንባትና ስራ መስራት ስላለባቸው የዝዋዩ ስራ ላይ ሲሆን የሻሸመኔው ግን እንደገና ፈርሶ በአዲስ መልክ እየተገነባ ስለመሆኑ አብራርቷል። በወላይታው የሆቴሉ ግንባታ ላይ የግብአት እጥረት ከፍተኛ  ተግዳሮት እንደነበረ ኃይሌ ተናግሯል። በዘጠኙም ኃይሌ ሆቴሎችና ሪዞርቶች በአጠቃላይ  1ሺ 800 ሰዎች ተቀጥረው እየሰሩ መሆኑን ለማወቅ ተችሏል፡፡

ኢትዮ ቴሌኮም በዘንድሮው መንፈቅ ዓመት 42.86 ቢሊዮን ብር አጠቃላይ ገቢ ማግኘቱንና አጠቃላይ የደንበኞቹ ብዛት 74.6 ሚሊዮን መድረሱን አስታውቋል፡፡
ኩባንያው ይህን ያስታወቀው ሰሞኑን  በስካይ ላይት ሆቴል የ2016 በጀት ዓመት የመጀመሪያ መንፈቅ የሥራ አፈጻጸም ሪፖርቱን ለመገናኛ ብዙኃን ባቀረበበት ወቅት ሲሆን፤ ሪፖርቱ ከሐምሌ 2015 እስከ ታህሳስ 2016 በጀት ዓመት ያለውን የሥራ አፈጻጸም የሚገልጽ መሆኑ ታውቋል፡፡  
በመንፈቅ አመቱ አጠቃላይ የደንበኞቹ  ብዛት 74.6 ሚሊዮን መድረሱን የጠቆመው ኩባንያው፤ ይህም  ከባለፈው በጀት ዓመት ተመሳሳይ ወቅት አንጻር የ4.7  ሚሊዮን ወይም የ6.7% እድገት ማሳየቱን እንዲሁም ከእቅድ አንጻር የ98.3% ውጤት መመዝገቡን አመልክቷል፡፡
በአገልግሎት አይነት ሲታይ የሞባይል ድምፅ ደንበኞች ብዛት 71.7 ሚሊዮን፣ የሞባይል ዳታና ኢንተርኔት ተጠቃሚዎች 36.4 ሚሊዮን፣ የመደበኛ ብሮድ ባንድ 688.3 ሺህ እንዲሁም የመደበኛ ስልክ ደንበኞች 834 ሺህ ሲሆኑ፤ የቴሌኮም ስርጸት (teledensity) መጠን 68.5% ማድረስ ተችሏል ብሏል፤ኢትዮ ቴሌኮም፡፡


”የደንበኞችን ቁጥር ለማሳደግ የተቻለው፣ ተሞክሯቸውን ለማሻሻል እንዲሁም ተደራሽነትን ለማስፋት፤ ተጨማሪ የሞባይልና የመደበኛ ኔትዎርክ ማስፋፊያ ሥራዎች በመሰራታቸው፣ተጨማሪ የአገልግሎት መስጫ ማዕከላትና የምርትና አገልግሎት አጋሮች በማካተት አዳዲስ ምርትና አገልግሎቶች ለገበያ በመቅረባቸው፣ የ5ጂ አገልግሎት በአዲስ አበባና በተወሰኑ የክልል ከተሞች እንዲሁም የደንበኞችን ተጠቃሚነት የሚያሳድጉ ወቅታዊነትን የተላበሱ 114 (64 አዳዲስ እና 50 ነባር) የሀገር ውስጥና የዓለም አቀፍ ምርትና አገልግሎቶችን በማሻሻል ለደንበኞች በመቅረባቸው ነው፡፡” ብሏል፤ ኩባንያው በመግለጫው፡፡ የአገልግሎት ጥራትን እንዲሁም የኔትወርክ ሽፋንና አቅምን ከማሳደግ አንጻር የኔትወርክ ማስፋፊያ የፕሮጀክት ሥራዎች በመከናወን ላይ ሲሆኑ ወሳኝ ተልዕኮ ላላቸው (Mission Critical)፣ በተመሳሳይ ወቅት(real time) መከናወን ለሚያስፈልጋቸው አገልግሎቶች እና internet of things የመሳሰሉ ቴክኖሎጂዎች በተግባር እውን እንዲሆኑ የሚያስችለውን 5G የሞባይል ቴክኖሎጂ አገልግሎት በተወሰኑ ከተሞች ለገበያ ማቅረቡንም አመልክቷል፡፡


 በግማሽ ዓመቱ በተደረገ የኔትወርክ ማስፋፊያ በ3G 678.2 ሺህ፣ በ4G 1.1 ሚሊየን እና በ5G 148.2 ሺህ በድምሩ 1.9 ሚሊየን ተጨማሪ ደንበኛ የሚያስተናግድ አቅም መፈጠሩን የጠቆመው ኩባንያው፤ በዚህም አጠቃላይ የሞባይል ኔትወርክ ደንበኛ ማስተናገድ አቅሙን 81 ሚሊየን ለማድረስ እንደቻለ ነው የገለጸው፡፡


በመንፈቅ አመቱ ከተሰሩ  የሞባይል ማስፋፊያዎች መካከል ለገጠር ቀበሌዎች የሚውል በ10 ክልሎች፣ ለ41 ወረዳዎች፣ 229 ሺህ ደንበኞችን ማስተናገድ የሚችሉ 41 የሞባይል ጣቢያዎች ተተክለው አገልግሎት መስጠት መጀመራቸውን እንዲሁም  በገጠር አካባቢ ባሉ 92 ነባር ጣቢያዎች ላይ የ3G ማስፋፊያ ስራዎች ተከናውነው አገልግሎት እንዲሰጡ መደረጉን አስታውቋል፡፡
ኢትዮ ቴሌኮም፤ የአገልግሎት አድማሱን በማስፋት፣ ቀጣይነት ያለው የደንበኞቹን አቅም ያገናዘበ አዳዲስና የተሻሻሉ ምርትና አገልግሎቶችን በማቅረብ እንዲሁም የተለያዩ የሞባይል ፋይናንስና የዲጂታል አገልግሎቶችን በማቅረብ በመንፈቅ ዓመቱ 42.86 ቢሊዮን ብር አጠቃላይ ገቢ በማግኘት የእቅዱን 98% ማሳካቱን አስታውቆ፤ ይህም ካለፈው በጀት ዓመት ተመሳሳይ ወቅት ጋር ሲነጻጸር የ8.86 ቢሊዮን ብር ወይም የ26% ብልጫ እንዳለው ጠቁሟል፡፡ ”የተገኘው ገቢ በአገልግሎት አይነት ሲታይ፤ የድምጽ አገልግሎት 41.8% ድርሻ ሲኖረው፣ ዳታና ኢንተርኔት 25.7%፣ ዓለም አቀፍ ገቢ 9.3%፣ እሴት የሚጨምሩ አገልግሎቶች 8.7%፣ የቴሌኮም አገልግሎት መጠቀሚያ መሳሪያዎች ሽያጭ 5%፣ ቴሌብር 2.5%፣ የመሰረተ ልማት ኪራይ 1.1%፣ እንዲሁም ሌሎች አገልግሎቶች 5.9% ድርሻ አላቸው፡፡” ብሏል፤ የኩባንያው መግለጫ፡፡
 የውጭ ምንዛሪ ከሚያስገኙ አገልግሎቶች 84.7 ሚ. ዶላር መገኘቱንና ይህም የእቅዱን 109% ያሳካ መሆኑን ኢትዮ ቴሌኮም አስታውቋል፡፡
 የቴሌብር አገልግሎት ከ41 ሚሊዮን በላይ ደንበኞችን በማፍራት የዕቅዱን 104% ማሳካቱን በመግለጫው ያመለከተው ኩባንያው፤  የግብይት መጠኑን  910.7 ቢሊዮን ብር በማድረስ አመርቂ ውጤት ማስመዝገቡን ጠቁሟል፡፡  የቴሌብር አገልግሎት ከተጀመረ አንስቶም በአጠቃላይ 1.7 ትሪሊየን ብር በኢኮኖሚው ላይ እያንቀሳቀሰ እንደሚገኝ አክሎ ገልጧል፡፡


በግማሽ ዓመቱ ከዲጂታል ኢትዮጵያ ግንባታ ጋር በተያያዘ 602 መንግስታዊና መንግስታዊ ያልሆኑ ተቋማት የአገልግሎት የክፍያ ስርዓታቸውን ከቴሌ ብር ጋር እንዲያስተሳስሩ  መደረጉንም ኩባንያው በመግለጫው አመልክቷል፡፡
ኢትዮ ቴሌኮም በመንፈቅ ዓመቱ ያጋጠሙትንም ተግዳሮቶች የዘረዘረ ሲሆን፤ በተለያዩ የሀገሪቱ  ክፍል ባጋጠመው የፀጥታ ችግር ምክንያት የአገልግሎት መቋረጥ፣በኔትዎርክ ሀብት ላይ የሚደርሱ አደጋዎች እንዲሁም የፋይበርና የኮፐር መስመሮች ስርቆትና መቆራረጥ፣ቴሌኮም ማጭበርበር፣ የግንባታ ስራ ግብአቶች እጥረት፣ የገበያ አለመረጋጋትና የሃይል አቅርቦት መቆራረጥ በዋናነት የሚጠቀሱ ተግዳሮቶች መሆናቸውን ጠቁሟል፡፡




የዘንድሮ የአፍሪካ እግር ኳስ ዋንጫ ይፋዊ ስፖንሰር ነው

የሞባይል ቴክኖሎጂ ብራንዶች አምራቹ ቴክኖ ሞባይል፤ ሰሞኑን ስፓርክ 20 ፕሮ ፕላስ (Spark 20 Pro+) የተሰኘ አዲስ ስማርት ሞባይሉን ያስተዋወቀ ሲሆን፤ ምርቱ በዘመናዊ ቴክኖሎጂ የተራቀቀ፣ እጅግ ከፍተኛ የካሜራ ጥራትና የፕሮሰሰር አቅም እንዲሁም ለረጅም ጊዜ መቆየት የሚችል ባትሪ፣ ማራኪ ቅርጽና ውበት ያለው የመጨረሻው የቴክኖሎጂ ውጤት መሆኑ ተጠቁሟል፡፡ኩባንያው ደንበኞች የላቀ የአገልግሎት ተሞክሮ እንዲኖራቸው የሚያስችለውን አዲስ  የስማርት ሞባይል ስልክ ሞዴሉን  በአዲስ አበባ ፍሬንድሽፕ ፓርክ በደማቅ መርሃ ግብር  አስተዋውቋል።

ቴክኖ ሞባይል አዲሱን ስፓርክ ፕሮ ፕላስ ሞዴል ባስተዋወቀበት ልዩ ዝግጅት የመንግስት ባለስልጣናት፣ የቴክኖ ሞባይል ኢትዮጵያ ከፍተኛ አመራሮች፣ የኢትዮጵያ አንጋፋ የእግር ተጫዋቾችና አመራሮች እንዲሁም የስፖርቱ ቤተሰብ የታደሙ ሲሆን፤ በኢትዮጵያ የስፖርቱ ዘርፍ እድገትና የአፍሪካ እግር ኳስ ዋንጫ ተሳትፎ እውን እንዲሆን ከፍተኛ ሚና የነበራቸውን የቀድሞ የኢትዮጵያ ብሔራዊ ቡድን ተጫዋቾች፣ አሰልጣኞችና የስፖርት ጋዜጠኞችን የማመስገኛ መርሃ ግበር ያካተተም ነበር። በስፖርቱ አለም ተወዳጅ ከሚባሉት ዝግጅቶች አንዱ የሆነውን የአፍሪካ ዋንጫ የእግር ኳስ ውድድር ይፋዊ ስፖንሰር የሆነው ቴክኖ ሞባይል፤ ይህን አዲሱን የሞባይል ሞዴል ከዚሁ የአህጉራዊ ስፖርት መርሀ ግብር ጋር በማስተሳሰር ቴክኖሎጂና ስፖርቱን ያጣመረ የማስተዋወቅ ልዩ ልዩ እንቅስቃሴዎችን በተለያዩ የአፍሪካ ሀገራት እያከናወነ እንደሚገኝ ለማወቅ ተችሏል፡፡

አዲሱ ስፓርክ 20 ፕሮ ፕላስ ሞዴል፤ በ108 ሜጋ ፒክስል አልትራ ሴንሴቲቭ (ultra-sensitive) የካሜራ ጥራት የተገጠመለት ሲሆን፤ በኤ.አይ (AI) ሲስተም በመታገዝ በየትኛውም አይነት የብርሀን መጠን በምሽት ሆነ በቀን ጥርት ያሉ ፎቶዎችን ማንሳት የሚያስችል ሲሆን፤ በከፍተኛ ፍጥነት የተለያዩ መተግበሪያዎችን ያለ እንክን እንዲያስተናግድ የሚያስችለው (G99 ultra boost) የተሰኘ ፕሮሰሰር ያለው መሆኑና 6.78 ኢንች አሞሌድ ስክሪን በ120Hz ሪፍሬሽ ሬት የሆነው ስፓርክ 20 ፕሮ ፕላስ ሲጠቀሙበት ያለምንም እንከን በቅልጥፍና አንዲያገለግል ያደርገዋል ተብሏል። የሞዴሉንም የመያዝ አቅሙን በመጨመር 256 ጂቢ ሚሞሪ በ16 ጂቢ ራም ጋር የቀረበ ሲሆን፤ 5000 mAh አቅም ያለው ባትሪ ከ33W ሱፐር ቻርጅንግ ሲስተም እንዳለውና በአጭር ጊዜ 100% ባትሪ ቻርጅ ማድረግ አቅም ያለው የስልክ ሞዴል ነው- ብሏል ኩባንያው ለአዲስ አድማስ በላከው መግለጫ፡፡

በዚህ በምረቃ ወቅት ንግግር ያደረጉት የቴክኖ ሞባይል ኢትዮጵያ ብራንድ ማኔጀር አቶ ኤሊክ ኋንግ፤ ‘’ይህ በላቀ ቴክኖሎጂ በልዩ መልክ የተመረተውን አዲሱ spark 20 pro+ በዚህ አህጉራዊ ውድድር ወቅት በማስተዋወቃችን ኩራት ይሰማናል። በኢትዮጵያ ብሎም በአፍሪካ እየጨመረ የመጣውን የቴክኖሎጂ ፍላጎት አለም ከደረሰበት የስማርት ስልክ ቴክኖሎጂ ጋር በማጣመር፣ የአህጉሪቷን እድገት ለማፋጠን ለሚደረገው ርብርብ የሚጫወተው ሚና ከፍተኛ እንደሚሆን አንጠራጠርም። ከዚም በተጨማሪ ድርጅታችን ቴክኖ ሞባይል ተወዳጅ የሆነውን አዲሱን ስፓርክ (spark 20 pro+) ስልክ ከማስተዋወቅ ባለፈ የብዙ እግር ኳስ ከዋክብት መፍለቅያ በሆነችው አፍሪካ የ2024ቱን የአፍሪካ የእግር ኳስ ዋንጫ ይፋዊ ስፖንሰር በመሆኑ ደስታችን ላቅ ያለ ነው።’’ ብለዋል።

· ዲሞክራሲ የሚፈተንበት ዓመት ነው ተብሏል
· በመላው ዓለም 4 ቢሊዮን ህዝብ ድምፁን ይሰጣል
· ከ60 በላይ አገራት ውስጥ ምርጫ ያካሂዳል
· በዓመቱ መጨረሻ ዲሞክራሲ መቀጠሉ አጠራጥሯል


የአንድ ወር ዕድሜ ብቻ ያስቆጠረው የፈረንጆች 2024 ዓ.ም በዓለማችን በታሪክ እጅግ በርካታ ምርጫዎች የሚካሄድበት ዓመት ነው። ምርጫ ብቻ ግን አይደለም። ተቃውሞ፣ ጦርነት፣ አምባገነንነት፣ ሥርዓት አልበኝነት አክራሪነት ወዘተ ዓለምን እንዳያናውጣት ተሰግቷል።  መረጃዎች እንደሚጠቀሙት በ2024 ዓ.ም ከ60 በላይ አገራት ውስጥ ምርጫዎች የሚካሄዱ ሲሆን፤ የዓለምን ግማሽ የሚወክል (4 ቢሊዮን ገደማ) ህዝብ ወደ ምርጫ ጣቢያ በማምራት፣ ለፕሬዚዳንታዊ፣ ለፓርላማና ለአካባቢያዊ ምርጫ ድምጹን ይሰጣል፡፡
ዘንድሮ የሚካሄዱ የዓለማችን ምርጫዎች ከግዙፉ የህንድ የበርካታ ቀናት የህግ አውጭ ምርጫዎች (በዓለም ላይ ትልቁ) እስከ የኢንዶኔዥያ ፕሬዚዳንታዊ ምርጫ (የዓለም ትልቁ የአንድ ቀን ምርጫ) እንዲሁም ትን የሰሜን ሜቆዶኒያ ፕሬዚዳንታዊ ምርጫ እንደሚደርስ ተጠቁሟል።
ኢኮኖሚስት ኢንተለጀንስ ዩኒቲ እንደሚለው፤ የ2024 ምርጫ በዓለማችን ሦስተኛ ዲሞክሲያዊ አገር በሆነችው አይስላንድ የሚካሄደውን ነፃና ፍትሃዊ ፕሬዚዳንታዊ ምርጫም ያካትታል፡፡ ከነፃና ፍትሃዊ ምርጫ ጋር እምብዛም ትውውቅ በሌለበት ሰሜን ኮሪያም ምርጫ ይደረጋል፡፡
ባንግላዲሽ 2024ን የተቀበለችው ለዓመቱ የመጀመሪያው የሆነውን አብይ ምርጫ በማድረግ ሲሆን፣ በውጤቱም ሼክ ሃሲና ለአራተኛ ተከታታይ የሥልጣን ዘመን በጠ/ሚኒስትርነት ተመርጠዋል፡፡ ችግሩ ግን ተቃዋሚ ፓርቲዎች ምርጫው ነፃና ፍትሃዊ አይደለም በሚል ቅሬታ ራሳቸውን ማግለላቸው ተዘግቧል፡፡
ራስዋን በምታስተዳድረው የታይዋን ደሴት ደግሞ ባለፈው ጥር 13 ቀን 2024 ዓ.ም ለአገሪቱ ወሳኝ የሆነው ፕሬዚዳንታዊ ምርጫ ተካሂዷል፡፡ ደሴቷን በሃይል ወደ ግዛቴ እጠቀልላሁ የሚለው የቻይና መንግስት ማስፈራሪያ በምርጫው ላይ ቁጥር ጥላውን ማጥላቱ አልቀረም፡፡  በምርጫውም የገዢው  ዲሞክራቲክ ተራማጅ ፓርቲ እጩ ሆነው የቀረቡት ላይ ቺንግ ቴቱ አሸንፈዋል፡፡ የእሳቸው ድል ግን ለቻይና አስደሳችና ተወዳጅ አልሆነም። እንደውም በታይዋንና በቻይና መካከል ያለውን ውጥረት እንዳያባብሰው ነው የተፈራው።
በመጪው የካቲት ደግሞ ኢንዶኔዥያ 277 ሚ. ህዝብ ባለቤት የሆነችው አዲስ ፕሬዚዳንት ለመምረጥ ተዘጋጅታለች፡፡ በዚሁ ወር ፓኪስታን የፓርላማ ምርጫ (የህግ አውጪዎች) የምታደርግ ሲሆን በዚህ መሃል ግን የተቃዋሚ መሪና የቀድሞው ጠ/ሚኒስትር ኢምራን ክሃን “የመንግስት ምስጢር አሾልከዋል” በሚል ተከሰው አሁንም በእስር ላይ ይገኛሉ፡፡ እሳቸው ግን ክሱን እንዳልፈፀሙ ይሞግታሉ፡፡
በመጋቢት ወር እንዲሁ ሩሲያውያን ፕሬዚዳንታቸውን ይመርጣሉ፡፡ ታዛቢዎች ግን በሥልጣን ላይ ያሉት ቭላድሚር ፑቲን በእርግጠኝነት እንደሚያሸንፉ ከወዲሁ ተንብየዋል፡፡ ለዚህም ምክንያቱም የምርጫው ሂደትና የመንግስት  መገናኛ ብዙሃን በቁጥጥራቸው ሥር መሆኑን ይጠቅሳሉ፡፡
“ፑቲን ምንም ዓይነት እውነተኛ ተቃዋሚ ሊኖራቸው አይችልም” የሚሉት የአውሮፓ ተሃድሶ ማዕከል ባልደረባ ኢያን ቦንድ፤ “እሳቸውን የሚደግፍ ድምፅ መሰጠቱን ለማረጋገጥ የሚያስፈልጉት ሁሉም የአስተዳደር ማሽኖች በቁጥጥራቸው ሥር ናቸው፤ እናም ቢያንስ እስከ 2030 ድረስ፣ ሌላ ስድስት ዓመት ፑቲን አብረውን ይዘልቃሉ” ብለዋል፡፡ በዚያ ላይ የተቃዋሚ ፓርቲ መሪ በእስር ቤት ነው የሚገኙት።
የዓለም ትልቋ ዲሞክራሲ በምትባለዋ ህንድ ደግሞ በሚያዚያና ግንቦት ወር የፓርላማ ምርጫዎች ይደረጋሉ፤ ጃናታ በቢሃራቲያ ፓርቲ (BIP)፤ በጠቅላይ ሚኒስትር ናሬንድራ ሞዲ ሥር፡፡ አንጋፋው ህንዳዊ የፖለቲካ ጋዜጠኛ ፑሽ ሳራፍ፤ ተቃዋሚዎች በምርጫው ለማሸነፍ እንደሚታገሉ ያምናል፡፡ ነገር ግን በአንድነት ከቆሙ ነው ይላል፡፡
ህብረት ካልጠፋና በአንድነት ካልታገሉ ግን ጠንካራ አደረጃጀት ያለውን የጠ/ሚኒስትሩን ፓርቲ የማሸነፍ ዕድል አይኖራቸውም-ብሏል (አንጋፋው ጋዜጠኛ)። ሰሜን 2 ቀን 2024 ዓ.ም ደግሞ በሜክሲኮ ፕሬዚንታዊ ምርጫ ይካሄል። ይህም ለአገሪቱ አዲስ ምዕራፍ የሚያበስር ነው ተብሏል፡፡ “ምክንያቱም ለመጀመሪያ ጊዜ ሴት ሜክሲኮን ልትመራ የምትችልበት እድል በመፈጠሩ ነው፡፡” ይላል-የሜክሲኮው የህዝብ አስተያየት ተንታኝ ፓትሪኮ ሞሬሎስ፡፡ የሜክሲኮ ገዢ ፓርቲ የቀድሞዋን የሜክሲኮ ሲቲ ከንቲባ ክላውድያ ሼይባምን በእጩነት መርጧል፡፡
ከግማሽ ቢሊዮን በላይ ህዝብ የሚወክለው የአውሮፓ ህብረትም የፓርላማ ምርጫ በሰኔ ወር እንደሚካሄድ ተጠቁሟል። የህዝብ አስተያየት እንደሚጠቁመው፤ ፈረንሳይን፣ ጀርመንንና ጣሊያንን ጨምሮ በበርካታ አገራት ውስጥ ለቀኝ ክንፍ ህዝበኛ ፓርቲዎች እንደገና ድጋፉ እያደረገ መጥቷል፡፡
“የቀኝ አክራሪ ወገኖች በአውሮፓ ምርጫ ጥሩ ቦታ ይኖራቸዋል፡፡ ይሄ ማለት ግን የአውሮፓን ፓርላማ እስከመምራት ድረስ አይደለም፤ የአውሮፓን ፓርላማ የሚመራ ማንኛውም ሰው ግን እነሱ የሚናገሩትንና የሚሰሩትን ከግምት ውስጥ ማስገባት ይኖርበታል፡፡” ሲሉ በለንደን ኪንግስ ኮሌጅ የዓለማቀፍ ፖለቲካ ፕሮፌሰር የሆኑት አናንድ ሜኖን ለቪኦኤ ተናግረዋል፡፡
ብሪታን በበኩሏ ከ2024 መጨረሻ በፊት ምርጫ ለማካሄድ ዕቅድ ይዛለች፡፡ የተቃዋሚው የሌበር ፓርቲ መሪ ኬይር ስታርመር፣ ለ14 ዓመታት የዘለቀውንና አምስት የተለያዩ ጠ/ሚኒስትሮች የተፈራረቁበትን የኮንሰርቫቲቭ አገዛዝን ከአመራርነት ለመግታት አልመዋል ምርጫውን በማሸነፍ፡፡
“ሁሉን ነገር የብሬክዚት ጦርነት ተቆጣጥሮት ነበር፤ ከዚያ ደግሞ ኮቪድ -19 ወረርሽኝ መጣ፤ አሁን የኑሮ ውድነት ቀውስ ውስጥ ገብተናል፡፡ የመንግስት አለመረጋጋት አጋጥሞና …. አለመረጋጋት ራሱ የፖለቲካ ጉዳይ ሆኗል” ብለዋል፤ ፕሮፌሰር ሜኖን፡፡
አሜሪካ ደግሞ በህዳር 2024 ዓ.ም በእጅጉ የሚጠበቀውንና በውዝግብ የተሞላውን ፕሬዚዳንታዊ ምርጫ ታካሂዳች፡፡ አሜሪካውያን ፕሬዚዳንታቸውን ከዲሞክራቱ ጆ ባይደን ወይም ከሪፐብሊካኑ ዶናድ ትራምፕ አንዱን እንደሚመርጡ ይጠበቃል፡፡ የጆ-ባይደን አስተዳደር ግን እስከ ምርጫው የሚያደርሰው አይመስልም። የብዙዎቹ ስጋትና ቀድሞወን ፕሬዚዳንት እስር ቤት በመወርወር ከምርጫው እንዳያስወጡት ነው። ሂደቱን ደግሞ ጀምረውታል። የፖለቲካ ተንታኞች ዓመቱ የምርጫ የመሆኑን ያህል ዲሞክራሲም የሚፈተንበት ነው የሚሉት ወደው አይደለም።
በ2024 የሚካሄዱ ምርጫዎች፣ ምርጫ በሚያካሂዱ አገራት ብቻ ሳይሆን ምርጫ በማያካሂዱም አገራት ላይ ተፅዕኖ ሊያሳድሩ እንደሚችሉ ሜኖን ይናገራሉ፡፡
“አዎ፤ ሁሉም ፖለቲካ አካባቢያዊ ነው፤ ነገር ግን ዓለማቀፋዊ አዝማሚያዎችም አሉ፡፡ ለምሳሌ የስደተኞች ጉዳይ (ኢሚግሬሽን) በዓለም ላይ በሚደረጉ በርካታ ምርጫዎች ላይ በብዛት ይገለጣል፡፡ በአውሮፓ ምርጫ ይገለፃል፤ በብሪታንያ ምርጫም ይገለጣል” ብለዋል፤ ሜሞን በሰጡት ፖለቲካዊ ትንተና፡፡
“እውን ዴሞክራሲ በአደጋ ላይ ነው?!”
ምንም እንኳን በ2024 በመላው ዓለም በ64 አገራት ምርጫ ቢካሄድም፤ ዲሞክራሲም የሚፈተንበት ዓመት ነው ይላሉ የፖለቲካ ተንታኞች፡፡ የዴሞክራሲ መገለጫ የሆነው ምርጫ በሚካሄድበት በዚህ ዓመት “ዴሞክራሲ በአደጋ ላይ ነው” የሚለው አነጋገር ተቃርኖ ግን አይደለም። ዓመቱን በምርጫ የጀመረችው ባንግላዲሽ፤ ጠ/ሚኒስትሯን ለ4ኛ ጊዜ የመረጠችው ተቃዋሚ ፓርቲዎች ራሳቸውን ከምርጫ ባገለሉበት ሁኔታ ነው ከምርጫው ቀደም ብላ የተቃዋሚ አባላትን፡፡
ሌላው ቀርቶ በዴሞክራሲ ብዙም የማትታማውና ለቀረው ዓለም አርአያ የነበረችው አሜሪካ፣ በዘንድሮ ምርጫ “ዴሞክራሲ በአደጋ ላይ ነው” እያለች ነው፡፡ የዴሞክራቱ እጩ ጆን ባይደንና የሪፐብሊኩ ዶናድ ትራምፕ እርስ በእርስ “የዴሞክራሲ ስጋት” በሚል እየተወራረፉ ነው፡፡ ሰሞኑን ፕሬዚዳንት ባይደን በምርጫ ቅስቀሳ ላይ “Democracy is on the ballot” ሲሉ ለደጋፊዎቻቸው ተናግረዋል፡፡ የኖቤል የሰላም ተሸላሚና የምርምር ጋዜጠኛ ማሪያ ሬሳ በቅርቡ እንደተናገሩት፤ “ዲሞክራሲ መኖሩን ወይም መሞቱን በ2024 መገባደጃ ላይ እናውቃለን፡፡”


Saturday, 27 January 2024 00:00

”የደጋ ሰው” በተሰኘው

አልበም ላይ ዛሬ ውይይት ይካሔዳል

”የደጋ ሰው” በተሰኘው አዲስ የሙዚቃ አልበም ላይ ውይይት እንደሚካሔድ፣ የኢትዮጵያ ሳይንስ አካዳሚ አስታወቀ፡፡
ዛሬ ከቀኑ 8  ጀምሮ ጉለሌ በሚገኘው የአካዳሚው የብላቴን ጌታ ኅሩይ ወልደ ሥላሴ የሥነጥበባት ማዕከል የሚደረገውን ውይይት፣ ደራሲና ሃያሲ ይታገሱ ጌትነት የሚመሩት ሲሆን፤ የሙዚቃ ባለሙያው ሰርፀ ፍሬስብሐት፣ መምህርና የሙዚቃ ደራሲው ኢዩኤል መንግሥቱ ለውይይት መነሻ የሚሆን ጽሁፍ ወይም ሃሳብ ያቀርባሉ ተብሏል፡፡ በውይይት መድረኩ ላይ ድምጻዊቷ የማርያም ቸርነትት እንደምትሳተፍ ታውቋል፡፡  

የአርቲስት ካሣሁን እሸቱ “ይሁን” የተሰኘ የሙዚቃ አልበም ትላንት መለቀቁ ተገለጸ፡፡ አርቲስቱ የአልበሙን መለቀቅ አስመልክቶ ባለፈው ሰኞ  በሸራተን አዲስ ጋዜጣዊ መግለጫ የሰጠ ሲሆን፤ ኪነት ኢንተርቴይንመንት ከአዲስ ሚውዚክ መልቲሚዲያ ጋር በመተባበር ይህን ”ይሁን” የተሰኘ  የድምጻዊ ካሣሁን እሸቱ የሙዚቃ አልበም ለማስመረቅ በዝግጅት ላይ መሆናቸው ተጠቁሟል፡፡በዚህ የድምጻዊው አዲስ የሙዚቃ አልበም ላይ በግጥም እራሱ አርቲስት ካሣሁን እሸቱ፣ አንጋፋው ድምጻዊ ቴዎድሮስ ካሣሁን (ቴዲ አፍሮ) እና መሰለ ጌታሁን፤ በዜማ ደግሞ አቤል ጳውሎስ፣ ድምጻዊ ካሣሁን እሸቱ፣ ቴዎድሮስ ካሣሁን (ቴዲ አፍሮ) የተሳተፉ ሲሆን፤ በቅንብር አበጋዝ ክብረወርቅ ሺዎታ፣ አቤል ጳውሎስ፣ ካሙዙ ካሣ፣ ሚካኤል ሃይሉና መሃመድ ኑርሁሴን፤ በሚክሲንግ ሰለሞን ሃ/ማርያምና ፍሬዘር ታዬ፤ በማስተሪንግ ደግሞ አበጋዝ ክብረወርቅ ሺዎታ ተሳትፈውበታል፡፡አዲሱ አልበም 15 በተለያዩ ስልቶች የተቀነቀኑ ዘፈኖችን ያካተተ ሲሆን፤ ድምጻዊው በዚህ አልበም ስለ ሃገር፣ ስለ ምስጋና  እና ስለ ተስፋ ማቀንቀኑ ተነግሯል፡፡
እዚህ ለመድረሴ የጋሞ አባቶች ምርቃት የመንገዴ ጠራጊ ነው ብሎ የሚያምነው ድምጻዊ ካሣሁን እሸቱ፤ ተወልዶ ያደገው በውቧ የመዋደድና የመከባበር ተምሳሌት በሆነችው አርባምንጭ ከተማ ነው፡፡
 አዲስ አበባ ከመጣ በኋላ የሙዚቃ ህይወቱን የጀመረው ቦሌ አካባቢ በሚገኘው ላየን ክለብ ከላፎንቴኖች ጋር በተዘጋጀው ፕሮግራም ላይ ነበር፡፡ ድምጻዊው በአንቲካ ባርና ሬስቶራንት ለ6 ዓመት፣ በመሣፍንት ቤት ደግሞ ለ5 ዓመታት በድምጻዊነት መሥራቱን ለማወቅ ተችሏል፡፡
የድምጻዊ ካሣሁን እሸቱ ”ይሁን“ የተሰኘ አዲስ የሙዚቃ አልበም፣ በትላንትናው ዕለት በራሱ የዩቲዩብ ቻናል (ካሣሁን እሸቱ ካስዬ) እንደሚለቀቅ ተጠቁሟል፡፡  

Sunday, 28 January 2024 20:22

ዘመናዊ ብልጦች

ዘመናዊ ብልጦች
ታጋይ እንጂ ትግል አይሞትም እያሉ
ታግለው ሲያታግሉ
ፎክረው የማሉ ታጋይ ሲፈነቸር
ትግሉም ፍግም ሲል
ይኸው ይኖራሉ።
(ሙሉነህ መንግሥቱ)

Sunday, 28 January 2024 20:20

አይን አዋጅ

ወላድ በድባብ ትሂድ
እንጂ ቆንጆ ሞልቶ ባሻገር፣
እኔ ዓይን አዋጅ ሆኖብኝ
እስቲ በምርጫ ልቸገር?
(መዓዛ ብሩ

አንድ ጊዜ አንድ የትግያ (Wrestling) ጥበብ አዋቂ፤ ለአንድ ተማሪው፤ “ና ትግያ ላስተምርህ” ይለዋል፡፡
ተማሪውም፤
“ምን ያህል የአስተጋገል ዘዴ ታውቃለህ?” ሲል ይጠይቀዋል፡፡
አስተማሪውም፤
“360 የትግያ አይነቶች እችላለሁ” አለው፡፡
“እነዚህን ሁሉ ለመማር ምን ያህል ጊዜ ይፈጅብኛል?”
“እሱ እንደቅልጥፍናህ ነው፡፡ አንዱ ጥበብ ከሌላኛው ጋር የሚያያዝ ነው፡፡ እስቲ ሞክረውና ከዚያ ጊዜውን ለመገመት ትችላለህ” ሲል ይመልስለታል፡፡
ከዚህ በሁዋላ መምህሩ ወጣቱን ማስተማር ጀመረ፡፡ የተወሰነ ዓመታት ፈጅቶበት ወጣቱ 359 የትግያ ጥበብና ዘዴዎችን ተማረ፡፡ የመጨረሻዋን ጥበብ ግን ሳይማር ቀረ፡፡ ወራትና ዓመታት እየገፉ በሄዱ ቁጥር ወጣቱ በትግያ እየተራቀቀ በገመድ ቀለበት ውስጥ የመጡ ተጋጣሚዎችን ሁሉ ተራ በተራ እየተጋጠመ እያሸነፈ የተዋጣለት አሸናፊ ሆነ፡፡ ዝናንም አተረፈ፡፡ በዚህም ከፍተኛ ኩራት ተሰማው፡፡
አንድ ቀን ሰው ሁሉ በተሰበሰበበት ለአስተማሪው፡-
“ሰማህ ወይ መምህር፤ እስከዛሬ ባስተማርከኝ ጥበብ በጣም ተራቅቄበታለሁ፡፡ ወደ ትግያ የገመድ ቀለበቴ የገቡትን ተጋጣሚዎች ሁሉ አንድ ባንድ እያነሳሁ አፍርጬ በአሸናፊነት ተወጥቻለሁ፡፡ አንተንም ቢሆን በማክበር ነው እንጂ ብገጥምህ እጥልሀለሁ” አለው፡፡
መምህሩም በዚህ በተማሪው ድፍረት በጣም ተናደደና፡-
“ለመሆኑ አሁኑኑ የትግሉ ገመዱ እንዲዘጋጅ ባደርግ ለመታገል ዝግጁ ነህ?” ሲል ጠየቀው፡፡
ተማሪውም፡-
“ከተዘጋጀሁ ቆይቻለሁ” አለው፡፡
መምህሩ በተማሪው መልስ በጣም ተበሳጭቷል፡፡
“እንግዲያው በል ና የአገሩ ሡልጣን ፊት ሰው ባለበት አደባባይ ላይ እንጋጠማለን” አለውና ወደ መታገያው የገመድ ቀለበት ውስጥ ገቡ፡፡
እንደተጀመረ ወጣቱ እየጮኸና እየዘለለ የመምህሩን ወገብ ጥብቅ አድርጎ ይዞ ሊጥለው ይወዘውዘው ጀመረ፡፡ ሆኖም አልጣለውም፡፡
እንደገና በሌላ ወገን ይይዘውና ዘርጥጦ ሊጥለው ይሞክራል፡፡ አሁንም አልሆነለትም፡፡
ወጣቱ 359ኙንም የመታገያ ዘዴዎቹን ተጠቅሞ ሊጥለው ሞክሮ ሳይሳካለት ቀረ፡፡ በኋላ መምህሩ መጠናከር ጀመረ፡፡ በመጨረሻም፡-
ወጣቱን በሁለት እጆቹ ወደ ላይ አንስቶ ቁልቁል ወደ መሬት ወረወረው፡፡ ወጣቱ ተሰባበረ፤ ሰውነቱ ደቀቀ፡፡
ተመልካቹ አካባቢውን በሆታ ሞላው፡፡
ሡልጣኑ መምህሩን አሰጠርቶ፡-
“ይሄ ወጣት በከተማችን የተነገረለትና በጣም እየጠነከረ የመጣ ነው፡፡ ማንም ሲጥለው አላየሁም፡፡ አንተ አርጅተሃል፡፡ አቅምህ ደክሟል፡፡ ታዲያ እንዴት ልትጥለው ቻልክ?” ሲሉ ጠየቁት፡፡
መምህሩም፤
“ሡልጣን ሆይ! ወጣቱን ሳስተምረው 359 ጥበቦችን ነው ያስተማርኩት፡፡ ይቺ አሁን የተጠቀምኩባት ጥበብ 360ኛዋ ናት፡፡ ይቺ የኔ የራሴ የክቴ ናት፡፡ ለእንዲህ ያለው ጊዜ ነው የምጠቀምባት፡፡ አንድ ጊዜ አንድ የቀስት ውርወራ አስተማሪ ያለ የሌለውን ጥበብ በሙሉ አስተምሮ ሲያበቃ አንዱ ተማሪው ውድድር ገጥሞ አሸነፈው፡፡ አስተማሪውም ‘ሳይቸግረኝ ያለኝን ዘዴ ሁሉ ሰጥቼ ነው ጉድ የሆንኩት!’ አለ ይባላል” ሲል በምሳሌ አስረዳቸው፡፡
***
ዘዴና ጥበብን ሁሉ ሙልጭ አድርገው ሰጥተው ባዶ መቅረት ኋላ ማጣፊያ ሊያሳጥር እንደሚችል ነው ከላይ ያለው አፈ-ተረት የሚነግረን፡፡ “ሁሉን ቢናገሩት ሆድ ባዶ ይቀራል” እንዲል የአበሻ ተረት፡፡ አሊያም በዚህ በውድድር ዓለም ተወዳዳሪህ ወይም ተፎካካሪህ ውሎ አድሮ ምን እንደሚያስብ በማጤን የክትህ የሆነ በልጦ መገኛ ዘዴ ሊኖርህ እንደሚገባ አስተውል ማለቱ መሆኑን እረዳለን፡፡ አንድም ብዙ ባሸነፍክ ቁጥር አቅምህን ሳትለካ መንጠራራት አሊያ ደግሞ አላስፈላጊ ግጥሚያ ውስጥ ገብቶ መቀናጣት ለምን አይነት ሽንፈት እንደሚዳርግ እንድናስተውል ይጠቅመናል፡፡ በሀገራችን በርካታ ፍልሚያዎች ወይ የእንቅስቃሴ ሂደቶች ውስጥ የባላንጣን ስስ ብልት በማየት በጎላ ፕሮፓጋንዳ ላይ ብቻ በማተኮር ሲደነቋቁሩ መክረም፣ ሀሰተኛ ቅስቀሳን በመደጋገም ከጊዜ ብዛት ይታመንልኛል ብሎ ማሰብ፣ ያገኙትን ትንሽ ድል እጅግ አጋኖ ግነን በሉኝ ማለት አልያም በጊዜያዊ ድል መኩራራት ወዘተ  ከግብ ላለመድረስ ጥቂት ተጠቃሽ ምክንያቶች ናቸው፡፡ ዳሩ ግን ከታሪክ ለሚማር ታሪካዊ እሴቶች ናቸው፡፡ ከቶውንም በሌሎች ላይ የምንሰነዝረው ትችትና ጥቆማ እኛ  ከምንሰራው ተጨባጭ ተመክሮ አንፃር ተግባራዊ ትርጉሙ ምንድን ነው የሚለው ጥያቄ ግንዛቤ ውስጥ ቢገባ ደግ ነው፡፡ በወንድምህ ዐይን ውስጥ ያየኸውን ጉድፍ…. እንዲል መፅሀፍ፡፡
ከማናቸውም ማህበራዊና ፖለቲካዊ ሂደት የምናገኘው ተመክሮ ጠርዝ ያለው መሰረት ይሆን ዘንድ ከ359ኛው ጥበብ ባሻገር 360ኛውን ማሰብ ተገቢ ነው፡፡ የሀገራችን ችግሮች ሁልቆ-መሳፍርት ናቸው፡፡ ሁልቆ-መሳፍርት ጥበብንና በብዙ ጭንቅላት ማሰብ ይጠይቃሉን፡፡ እኔ ብቻ ነኝ መፍትሄ ልሰጣቸው የምችለው ማለት ብዙ አያራምድም፡፡
ሆደ-ሰፊና ተቻቻይ ከሁሉ ጋር ተባብሮ፣ ተግባብቶ ሙያን አክብሮ ልምድን በአግባቡ ተጠቅሞ መንቀሳቀሰስ አግባብ ነው፡፡ ያቅም፣ ካቅም በላይም አሊያም ካቅም በታች፣ አቅሜ ነው ብሎ መዋሸት ቀኑ ሲደርስ “ምላጭ የዋጠ ማስወጣቱ ይጨንቀዋል” የሚባለውን ተረት ነው የሚያረጋግጠው፡፡
አያሌ በሀገርም ደረጃ፣ በዓለምም ደረጃ የምንገባቸው ውሎች የምናልማቸው ትርፎች፣ የምናቅዳቸው ዲፕሎማሲያዊ አካሄዶች፣ “እዚያ ቤት እሳት አለ” ብለን የምናጤናቸው ሊሆኑ ይገባል፡፡ ዐይነ-ውሃቸው የሚያምር ወይም ከጊዜያዊ ጣር የሚያላቅቁን የሚመስሉ አያሌ ጉዳዮች ኋላ የማይያዙ የማይጨበጡ እዳዎች፣ ውል-የሌላቸው ችግሮች እንዳይሆኑ መጠንቀቅ ይገባል፡፡ አብዛኞቹ የኢኮኖሚ መስተጋብሮች ረጋ ተብለው ሲታሰቡ፣ ሙስናዊ ቀዳዳዎቻቸው የበዙ መሆናቸው ብቻ ሳይሆን፣ እያንዳንዳቸው ቀዳዳዎች እያደር እየሰፋ የሚሄዱ እንዳይሆኑ ግለሰቦች ላይ ከጣለው ፖለቲካዊ እምነት ባሻገር በሀገር መንፈስ ማውጠንጠን፡፡ ሲሞን ቦሊቫር የተባለ የአዲሲቱ የላቲን አሜሪካ ሪፑብሊክ መሪ “በሦስቱ ጥምር ችግሮች ማለትም - ድንቁርና ጭቆናና ሙስና ተጠፍረን ታስረን፣ ትምህርት፣ ሥልጣንና  ሥነምግባር ሊኖረን አልቻለም፡፡ እናም የተማርነው ባልሆኑ መምህራን ስለሆነም ያገኘናቸው ልምዶችም ሆኑ ያናናቸው ምሳሌዎች ወደ ጥፋት የማምራት ባህሪ ነው ያላቸው፡፡ ከጉልበት የበለጠ በመታለል ተጠቅተናል፡፡ ሙስናም ከአጉል አምልኮ የበለጠ ቁልቁል አርጎናል፡፡…. ምኞትና ተንኮል ሁነኛ የፖለቲካ፣ የኢኮኖሚ ወይም የሲቪክ እውቀት የሌላቸው ሰዎች፣ ልምድ የለሽና በቶሎ አማኝ ያደርጋቸዋል፡፡ ቅዠቶቹን እውን አድርገው እንዲያዩ ያደርጋቸዋል፡፡ ፈቃድን ከነፃነት ያምታታባቸዋል፡፡ ክህደትን ከጀግንነት ያወነባብድባቸዋል፡፡ በቀልንም ከፍትህ ያምታታባቸዋል” ይላል፡፡ ከዚህ ይሰውረን ማለት ደግ ነው፡፡
ነባራዊና እሙናዊውን ቀና መንገድ ይዞ መጓዝ ከበሽታ ያድነናል፡፡ ከኢኮኖሚ ድቀት ያወጣናል፡፡ ከስህተታችን እንድንማር ያደርገናል፡፡ ከሁሉም በላይ ግን የገባነውን ቃል እንድናከብር ያግዘናል፡፡ ዞሮ ዞሮ ግን የምንለው ከምናደርገው ካልተገናኘና አልፎ ተርፎም አገርና ህዝብን የሚጎዳ ከሆነ “ምላስ ደህና ቦታ ተቀምጣ፣ ጭንቅላት ታሰብራለች” የሚለውን አባባል ነው የሚተረጉም፡፡