Administrator

Administrator

  ‹የጥንታዊ ኢትዮጵያን ጥበብ› የሚዳስሱ መረጃዎችን ለመሰብሰብ ስውተረተር፤ ‹Encarta 2009›ን ስለ ኢትዮጵያ ፍልስፍና ምን እንደያዘ ጠየቅኩት:: የአውሮፓ ነው ያለውን ከጥንታዊት ግሪክ ጀምሮ እስከ ዘመናዊ አሜሪካ ድረስ ያሉ የፍልስፍና ዓይነቶችን ዘርዝሮ አቀረበልኝ፤ ወደ ህንድና ቻይናም ሔዶ አማረጠኝ፤ ወደ መካከለኛው የእስልምና ዓለም ፍልስፍናም ወስዶ አስጎበኘኝ። ምንም እንኳን በዚህ መልክ ቢያማርጠኝም፤ እኔ ግን ‹ጥያቄዬ አልተመለሰም› አልኩት፡፡ ሐቀኛው Encarta እንኳን በኢትዮጵያ በአጠቃላይ በአፍሪካ፣ ፍልስፍና መኖሩን እንዳማያውቅ እቅጩን አረዳኝ፡፡ ይህም የቀድሞው የቀዳማዊ ኃይለ ሥላሴ ዩኒቨርስቲ ፕሬዝዳንት የነበሩት ዶክተር አክሊሉ ሀብቴ የተናገሩትን አስታወሰኝ፡፡
ዶ/ር አክሊሉ፣ ለአሜሪካን ኮንግረስ የአፍሪካ ክፍል በአቀረቡት የመወያያ ሐሣብ፤በእ.ኤ.አ.1958 በካይሮ ላይ ‹Mutual appreciation of western & Eastern cultural values› በሚል ርዕስ በተካሔደ ጉባኤ፤ የአፍሪካ አስተምህሮ አለመነሳቱ አስገርሟቸው ‹አፍሪካ የት ናት?› የሚል ጥያቄ ለመጠየቅ መገደዳቸውን አንስተው፣ የተሰጣቸው መልስም ‹አፍሪካ ያላት ማሐይም ማኅብረሰብ ነው› የሚል ዓይነት እንደነበር አስታውሰዋል፡፡ እኔም Encarta ሐቀኛ መልሱን ከነገረኝ በኋላ ብዙ ጥያቄዎች ተግተለተሉብኝ፡፡
ከጥያቄዎቹ መካከል አንዱ፤ ‹ለምን የእኛ ዕውቀት ሳይመዘገብ ቀረ?› የሚል ነው፡፡ Encyclopedia of Philosophy የሚለውን ባለ አሥር መድበል የዕውቀት መዝገብ አገላበጥኩት፡- ‹ከየት ላምጣልህ?› የሚል መልስ ነበር ያገኘሁት፡፡ ጉድ! ብላችሁ ሃዘን እንዳትቀመጡ፤ ሰጋሁ፡፡ ቢያንስ እነ ዘርዓ ያእቆብን አለማወቁ አይገርማችሁም? እውን ኢትዮጵያ፤ የእኔ የምትለው የራሷ ጥበብ የላትም? ነው እንዳይታወቅ የተፈለገበት ምክንያት አለው? ግን ለምን? ኢትዮጵያ አሁን እንዳለችበት ሳትሆን በፊት በተለይም በጥንት ዘመናት የሥልጣኔዎች ምንጭ የነበረች ሀገር ናት። በቅርብ ጊዜያት የተከሰቱ ጉድፈቶችን ለመዛግብተ ቃሎቻቸው ማብራሪያ እንደ ምሳሌ ለማስቀመጥ የፈጠኑ አውሮፓውያን፤ ለምን በአጠቃላይ የአፍሪካን በተለይም የኢትዮጵያን ፍልስፍና መዝግበው ለማሳወቅ ሳይችሉ ቀሩ? ከእነ ደካርትና ካንት ፍልስፍና ጋር ይመሳሰላል የሚባለውን የዘርዓ ያዕቆብን ፍልስፍና ያላካተቱበት ምሥጢሩ ምንድነው? አለማወቅ? ዘረኝነት? ወይስ ሌላ ጉዳይ?
 የኢትዮጵያ ፍልስፍና ማጠንጠኛ
ከላይ የጠቀስኳቸውን ጥያቄዎች እያብሰለሰልኩም፤ ‹ራሱ ፍልስፍና ምንድን ነው?› የሚል ጥያቄ መጣብኝ፡፡ በጣም የከነከናችሁን ጥያቄ ስትጠይቁ፣ መልሱን ቶሎ ካላገኛችሁ የበለጠ ጥያቄ ይጎለጎልባችሁ የለ? ስለዚህ የፍልስፍና ምንነትን ማብሰልሰል ጀመርኩ፡፡ ፍልስፍና በነጠላ ትርጉሙ፤ ‹ጥበብን ማፍቀር› ማለት እንደኾነ  መጀመሪያ ቃሉን ተናገረው ከተባለው ከፊጣጎረስ (Pythagoras) መረዳት ችያለሁ፡፡ ሶቅራጥስም የፍልስፍና መሠረቱ መደነቅ መቻል መኾኑን ነግሮኛል፡፡ በጥበብ ፍቅር ተነድፎ በመደነቅ ምርምር የሚደረገውም ትክክለኛው እውነት ጋር ለመድረስ መሆኑንም ተረድቻለሁ፡፡ እና ኢትዮጵያውያን በታሪካቸው የዚህ ዓይነት ጥበብ አልነበራቸው? ይህንን ለማረጋገጥም የኢትዮጵያውያንን የጥንታዊ የትምህርት መስኮች (ጉባኤያት) መዳሰስ አስፈላጊ ኾኖ አገኘሁት፡፡ በዚህም ‹የኢትያጵያ ፍልስፍና ምን ዓይነት ነው?› ለሚለው ጥያቄ መልሱን ማፈላለግ ጀመርኩ፡፡ ከዚያም የሚከተሉት ነጥቦች የኢትዮጵያውያን ጥበብ ዋና ዋና ማጠንጠኛዎች መስለው ታዩኝ፡፡
 ሃይማኖት የጥበብ መነሻና ማዕቀፍ
የኢትዮጵያ ጥበብ መሠረቱ ዕውቀት ሳይሆን ሃይማኖት (እምነት) መሆኑን ተረዳሁ፤ ስለሆነም ‹የጥበብ መጀመሪያ እግዚአብሔርን መፍራት ነው።› ይላል፡- በኢትዮጵያ የተመለከትኩት ፍልስፍና። በዚህም የተነሳ፤ ‹በእግዚአብሔር መኖር ላይ ተማምኖ መፈላሰፍ ይቻላል? ወይስ አይቻልም?› የሚለው ጥያቄ መጥቶ ድንቅር አለብኝ፡፡ ለዚህ የሚሆን መልስ ሳፈላልግም፣ አብዛኞቹ የጥንታዊት ግሪክ ፈላስፎች፣ የአንድ አምላክ መኖርን የሚደግፉ ሆነው አገኘኋቸው፡፡ እነ ኤራቅሊጠስ፣ ዜኖፎን፣ ሶቅራጥስ፣ ፕሌቶ፣ አርስጣጣሊስና ሌሎችም አጠራራቸው ቢለያይም፣ በእግዚአብሔር መኖር ግን እንደሚስማሙ ሳያብሉ መሰከሩልኝ። ለማጠናከር ብዬ ወደ ሮማያውያን ተሸጋገርኩ። እነ አውግስቲን ኋላም እነ ቶማስ አኳይነስ “የፍልስፍናችን መሠረትና ጉልላት የእግዚአብሔር መኖር ነው” ብለው መለሱልኝ፡፡ ምስክር በሦስት ይፀናል ብዬ ወደ ዘመናዊያን ፈላስፎች ተጠጋሁ፤ እነ ደካርት፣ በርክሌይ፣ ካንትና መሰሎቻቸው የፍልፍናችን መሠረት እግዚአብሔር ነው አሉኝ። ከዚህ በኋላ እንግዲያውስ፣ የኢትዮጵያውያንም ጥበብ መሠረቱን ‹እግዚአብሔርን መፍራት› ማድረጉ ከፍልስፍና ውጭ አያስወጣውም አልኩኝ። በእምነት ላይ የተመሠረተ ፍልስፍና አይኖርም ያለው ማን ነው?
 እንደውም ፍልስፍና በእምነት ላይ ሲመሰረት አሳማኝነት ይኖረዋል ብዬ ገመትኩ፤ እምነት አልባ ፍልስፍና ግን መሠረቱ አጨቃጫቂ ነውና፤ አጨቃጫቂ ነገርም ተቀባይነት አይኖረውም፡- የሚል እምነት ሰረፀኝ፡፡ ምክንያቱም የፍልስፍና መሠረት እምነት ነው ካልን፤ የእምነት ዋናው መሠረትም፣ የእግዚአብሔር መኖር ነው፤ እግዚአብሔር ደግሞ በባሕርዩ ፍጹም ስለሆነ ሌላ አያስፈልገውም፤ የአስተሳሰብ ሁሉ መደምደሚያ ነው፡፡ ነገር ግን ፍልስፍና የእምነት መሠረት ከሌለው በምን መነሻ መስማማት ይቻላል? ስለዚህ የኢትዮጵያውያንም ፍልስፍና በእምነት ላይ መመሥረቱ አስተውሎታዊ ነው እንጂ አለማወቅ አይደለም፤ ብዬ ወሰድኩት፡፡
 የጥበብ በሥነ ምግባር መቃኘት
ሁሉም ጥበባቸው በሥነ-ምግባር የተቃኘ መሆኑን ዐየሁ፤ ለዚህም የተረጎሟቸው የታዋቂ ፈላስፎች ጽሑፎች ሳይቀሩ በምስክርነት አረጋገጡልኝ፡፡ አንጋረ ፈላስፋን (የፈላስፎች አነጋገር) አገላብጬ ተመለከትኩት፤ የብዙ ፈላስፎች ሥነ ምግባራዊ ንግግር ወይም መልካም ምክር በኢትዮጵያውያን መንፈስ ተቃኝቶ ተሰብስቦበታል፡፡ እንደውም አብዛኞቹ የመጽሐፉ ጥቅሶች፤ ኢትዮጵያውያን ሊቃውንት የራሳቸውን ፍልስፍና ደብቀው በሌሎች ፈላስፎች ስምና ባልታወቁ ፈላስፎች መልክ የሰገሰጉባቸው መሆናቸውን ጠረጠርኩ፡፡ ጥርጣሬዬ ያለምክንያት አይደለም፤ ኢትዮጵያውያን ሊቃውንት ትህትና ስለሚያጠቃቸው ዐዋቂ ሰው መስለው መታየት እንደማይፈልጉ ከጻፏቸው የሃይማኖት መጻህፍት   ተገንዝቤአለሁ፡፡ ስለዚህ ይህም ጥርጣሬ የኢትዮጵያውያንን የትህትና ልምድ በማየት የመጣ ነው፡፡ በተጨማሪም የዘርአያዕቆብንና የወልደሕይወትን ፍልስፍናዊ መጣፎች ተመለከትኩ፤ በዋናነት በሥነምግባር ዙሪያ የሚያጠነጥኑ ወይም በሥነ ምግባር ፍልስፍና የተቃኙ ናቸው፡፡ ሥነ-ምግባር ደግሞ አንዱና ዋናው የፍልስፍና ትምህርት ክፍል መሆኑን ዐውቃለሁ። እንደውም ሥነ-ምግባር አልባ ፍልስፍና ሰብዕና አልባ ዕውቀት እንደሚሆን አልጠራጠርም፡፡ ስለዚህ የጥንት ኢትዮጵያውያን ፍልስፍና በሥነ ምግባር ገመድ መሸበቡ፣ መልካምና ጥሩ ፍልስፍናዊ ዕይታ መሆኑን አጤንኩኝ፡፡
  የጥበብ ዕምቅነት፣ ኅብራዊነትና አመሥጥሯዊ ትርጓሜ
ፍልስፍናቸው በዋናነት በኅብር ትርጓሜያት የሚፈታ መሆኑንም የተመለከትኩት መለያው ነው፡፡ በመጀመሪያ ቅኔዎቻቸውን ተመለካከትኩ፤ የሚደንቁ ዕይታዎችንና ልዩ አቀራረቦችን ሳገኝ ‹ይህማ የትም የማይገኝ የኢትዮጵያውያን ብቸኛ ፍልስፍና ነው!› እስከማለት ደረስኩ፤ ተደንቄ፡- መፈላሰፍ ልጀምር! ቅኔያቸው ሥጋና ነፍስ የተዋሐዱበት እንጂ በአጥንትና ሥጋ ብቻ የተወሰነ አይደለም፤ ሰው ሕይወት ዘርቶ የሚንቀሳቀሰው ነፍስ ያለው ከሆነ ነውና፡፡ ይህ ደግሞ የሚገለፀው በኅብርነት ነው፡፡ ተፈጥሮ የተሠራችው ታምቃ በኅብርነት ስለሆነ የኢትዮጵያም ጥበብ ኅብርነት ማጠንጠኛው መሆኑን ታዘብኩኝ፡፡ ይህንን በሚመለከት የኔታ ዓለማየሁ ሞገስ፤ “መልክዐ-ኢትዮጵያ” በሚለው መጽሐፋቸው፡-
‹የኅብር አገር ጎጆ መግቢያና መውጫው፣
ሊቃውንት የሠሩት ኹለት በር አለው፤
ምንም ኹለት ቢኾን ሦስት አራትም፣
ጠባብ ስለኾነ ደንቁር አይገባም፡፡› ብለዋል፡፡
የትርጓሜ መጻሕፍታቸውን ቃኘሁ፤ እያጋጩና እያነጻጸሩ ሲያብራሩና ትክክለኛውን አንድምታ አንጥረው ሲያወጡ ዐይቼም፤ ‹እና ከዚህ በላይ ፍልስፍና ምን ዓይነት ነው!?› ብዬ ራሴን ጠየቅሁ፤ ለምንስ ትርጉም አስፈለገ? አልኳቸው በጨዋነቴ፡፡ ‹ፊደል ይገላል፤ ምሥጢር ግን ሕይወትን ይሠጣል› ብለው የተሸፈነውን፣ ነፍስ የሆነውን መልዕክት ለመረዳት፣ መተርጎም እንዳለበት አስረዱኝ፡- “አዬ! የልጅ ነገር፤ አሁን ይኼ ይጠየቃል!” ብለው እኮ ነው፡፡
እንዲሁም አባባሎቻቸውን፣ ምሳሌያዊና ፈሊጣያዊ ንግግሮቻቸውን፤ እለታዊ ጨዋታቸውን በማየት ድንቅ ለዛቸውንና ዐስተውሎታዊ ንግግራቸውን፣ በዐጭሩ እነሱ ‹እንደ ወርቅ አንከብሎ እንደ ሸማ ጠቅልሎ› እንደሚሉት ሆኖ አገኘሁት። በዚህ ላይ ወሬ አምሮኝ፣ በልጅነት ጠጋ ጠጋ ብላቸው እኮ፣ ለልጅ በሚገባ መልኩ ‹ዕንቆቅልህ!› ማለታቸው አይቀርም! እኔማ ምን እመልሳለሁ ‹ምን ዐውቅልዎት!› ከማለት ውጭ፡፡ ጉድ! ምሥጢር እየሣበኝ እኮ ብዙ ወሸከትኩ፡፡ በጥቅል ላውራ፤ አዎ በጥቅሉ በኢትዮጵያውያን ፍልስፍና፤ መንፈሳዊነት የሌለው አስተያየት የለም፤ መንፈሳዊነቱም ያለ ሥጋዊ ግዙፍ ነገር አይገለጽም፡፡ ስለዚህ ኅብረ-ነገር (ኅብረ-ፍልሰፍና) የኢትዮጵያውያን ዕውቀት ድረ-ማግ ነው፡፡
  አስማትም ጥበብ ነው!
ከዚህ ሌላ ስለ ደብተራዎች ድንቅ ግብር (አስማተ-መተት) አንስቼ አላውራ እንጂ እነሱን እኮ ጠላት አይደፍራቸውም! አልተወራላቸውም እንጂ ኢትዮጵያ ከጥንት ጀምሮ ነፃነቷን ጠብቃ የኖረችው በእነሱ የመተት ጥበብ ጭምር ነው! … ካላመናችሁ ባለ ቅኔ ‹ገሞራው›ን ምስክር ልጥራ፡- የደብተራውን ግብር ያውቃልና እንዲህ አለ፡-
‹…በሩቅ አነጣጥሮ- በራዳር አስማቱ፣
ቶርቦዶ የሚያደርግ- ባንደርቢ ድግምቱ፣
ካድማስ የሚያወርድ- ሳተላይት ምትሃቱ፣
ድባቅ የሚመታ- ባዙቃ አንደበቱ፣
ድምጥማጥ አብንኖ- ጠላት አርጊ ከንቱ፣
ታላቅ ግብር(Role) ነበረው- ደብቴ ታጋይ ብርቱ፣…..›
(አቢሲኒያ መጽሔት ቅጽ 1፣ ቁጥር 16 ጥር 1993)
በሞቴ ስለ ደብተሮች አንድ ታሪክ ላውራ! የልጅ ወሬም ቢሆን ያዳምጡኝ፡፡ ወሎ ውስጥ ነው አሉ፡- ላስታ አካባቢ፡፡ አንድ መሪጌታ ናቸው፡- ድብትርናቸው ያልታወቀባቸው ሊቅ፡፡ የመጀመሪያ ልጃቸውን የቀለም ቀንድ ያደርጉታል፤ አጅሬው ከሳቸውም አልፎ ጠቢብነትን ይዞ እቤቱ ‹ከች!›። አንድ ቀን ታዲያ እናቱ ክሽን ያለች ዶሮ ወጥ ለአባወራዋ ትሠራለች፤ አባት ግን ከልጅ ጋር መሻማት አልፈለጉም፡፡ ስለዚህ ልጃቸው ከቤት የሚወጣበትን ዘዴ ቀይሰው ዘመድ ጋር መልዕክት ይልኩታል፤ ይች ዘዴ የገባችው ልጅ ደግሞ በድግምቱ ድስቲቷን ቆልፏት ይሔዳል፤ ማን ወንድ ይክፈታት! አባት ተናደዱ፤ ልጁም መልዕክቱን አድርሶ መጣ፡፡ የተናደዱት አባት ግን ልጃቸው ገና በሩ ላይ ሲገባ ዐሠሩት፡- መውጣት አይችል መግባት አይሆንለት፤ የበር መዝጊያ መስሎ ቆመ፡- እንሞካከር ማለት እኮ ነው - በደብተራኛ፡፡
እሱስ ቢሆን ያስመሰከረ ሊቅ አይደለ? አባቱን ዐያቸው፤ ፊት ለፊቱ በአንድ እግራቸው መሬት እረግጠው በሌላው ደግሞ ካልጋው ጠርዝ ላይ አንፈራጠው ይመለከቱታል፡፡ ሊቁ ልጅም ጦርነቱን ዝም ብሎ አልተሸነፈም፤ አባቱን ከመሬትና ካልጋ ጋር ጠፈራቸው፡- መዘዋወር የለ! መንቀሳቀስ። አሁን ተግባቡ፤ “በል ልጄ ፍታ! ልፍታ!” አሉ አባት፤ ተፈታተው አብረው በሏታ! ክሽንዋን የዶሮ ወጥ። ጎበዝ ለጎበዝ ከተገናኘ ይከባበራል፡፡ አዩልኝ፤ ይህንን ጥበብ! የመስተፋቅር ጥበባቸውንማ ሁሉም የሚያውቀው ነው! ምን አወራዋለሁ!፡- ካስነኩ በቃ! በፍቅር ክንፍ ነው፡- እንቅልፍ የለ! ምግብ አያሰኝ! ዝም ብሎ በፍቅር መንፏቀቅ!
ከፊደል እስከ ሰዋሰው ሥርዓት ያለው ጥበብስ?
በኢትዮጵያ ሊቃውንት ዕውቀት መዋቅራዊ ጥበብ ተገረምኩ፡፡ ከፊደል ገበታ ጀምሮ እስከ ሰዋሰዋዊና አጠቃላይ የቋንቋ መዋቅር ስልታቸውን ሳይ መልሴ ምን ሆነ? ‹ዕፁብ! ዕፁብ! ውእቱ!› የፊደል ገበታ እኮ የኢትዮጵያ ማንነት የተጻፈበት ካርታ ነው፡- የሚያነበው ቢገኝ:: ስለሆነም ነው ሊቁ አስረስ የኔሰው፤ ‹“ፊደል ሐውልት ነው … ፊደል መልክ ነው … ፊደል አባት ነው … ፊደል ልጅ ነው … ፊደል ወሰን ነው … ፊደል ዓላማ ነው … ዓላማም የኩራት ምልክት ነው፡፡ ኩራትም ነፃነት ነው፡፡ … የማንኛው ነገር መጠቅለያ ፊደል ነው፡፡” ብለው የመሰከሩት፡፡ (አስረስ የኔሰው፤ “የካም መታሰቢያ የኢትዮጵያ ፊደል መሠረትነት መታወቂያ” 1951 ዓ.ም)፡፡ አረ ለመሆኑ! የእኛን ፊደል የሚያስንቅና የሚቀድም የዓለም ፊደል (አልፋ ቤት) ይምጣና እስቲ ይወዳደር ብዬ ልፎክር እንዴ? ይኸው ፎከርኩ!
የሰዋሰው መዋቅሩም እኮ የተፈጥሮ ግልባጭ ነው፤ ምን ልበል!:- ሰማይና መሬት በዕውቀት የተገናኙበት መሰላል ማለት እንጂ፡፡ በአዕማዳት ቆሞ፣ በአለቃ ተደራጅቶ፣ በሠራዊት የሚጠበቅ፣ በመራሂያን የሚፍታታ፣ በዓቢይና በንዑስ አግባባት እየተዋሐደና እየተበተነ የሚታሠር አስደናቂ የዕውቀት ድርጅት ነው እኮ ሰዋሰዋችን! ስለዚህ የዕውቀት ድርጅት እኔማ ምን እላለሁ? ሊቃውንቱ ቢያወሩት ይሻላል እንጂ! የእኔ ግብር ‹አባ በሌሉበት…› ዓይነት ነው፡፡
በአጠቃላይ ስለ ባህላችን ልናገር እንዴ? ስለ ትውፊታችን ልመስክር እንዴ? ስለ ገዳ ሥርዓት፣ ስለ ሥነ መንግሥት፣ ስለ ዘመን አቆጣጠራችን፣ … ስለተጠየቅ ልጠየቅ፣ ስለ በልሃ ልበለሃ--- ክርክር ላውራ እንዴ? ጊዜ አይበቃማ! ባላዋቂነት ይበላሻላ! አቅም የለማ!... በዐጭሩ የኢትዮጵያውያንን አስደናቂ ፍልስፍና ተመልክቼ፣ ጥበበኛነታቸውን ማረጋገጥ ቻልኩ፡፡ ከዚያም እንዲህ አልኩ፤ ‹እኔ የዚህን ያህል ዐይቼ፣ ፍልስፍናቸው ከማረከኝ፣ ዐስተዋይ የፍልስፍና ሊቅ ቢፈትሸውማ! ምን ሊል ነው?› ግን እስከዛሬ በአግባቡ ያልተፈተሸው ለምንድን ነው? መልሱን በአግባቡ ማግኘት አልቻልኩም፡፡ በወፍ በረር የሞካከሩት እንዳሉ ግን መመልከቴን አልሸሸግም፡፡
ማሳረጊያ
ሐሣቤን ልቋጭና ልሰናበት፡፡ በእኔ አቅም የኢትዮጵያውያንን አስገራሚ አስተውሎቶች፣ የጥበብ ፍቅር፣ እውነት ለማግኘትና ለማረጋገጥ የሚሔዱበትን እርቀት ዐይቼ ተደንቄያለሁ፡፡ እኔ እንደተረዳሁት ኢትዮጵያውያን የሥልጣኔው ምንጭ ነበሩ፡፡ የሥልጣኔ ምንጭ ለመሆን የቻሉት ደግሞ የራሳቸው ዐተያይ፣ አስተምህሮና የዕውቀት ክምችት ስለነበራቸው ነው፡- ገና ጥንት፡፡ ሊኖራቸው ከሚችለው ዕውቀት ውስጥ ደግሞ ፍልስፍና ቅድሚያውን ይይዛል፡፡ ስለዚህ ‹ኢትዮጵያውያን የራሳቸውን ፍልስፍና ያዳበሩ ሕዝቦች ነበሩ፤ አሁንም ናቸው› ብዬ ደመደምኩ፡፡
 ሆኖም በውስጤ ለተፈጠረብኝ ‹ለምን?› የሚል ጥያቄ፣ መልስ ማግኘት አልቻልኩም፡፡ የእኛን ፍልስፍና፤ ዓለም አቀፍ መዝገበ ቃላትና ዕውቀተ መዝገብ የማያውቁት፣ በእኛ ስንፍና ሳይሆን አይቀርም፡፡ ወይስ የእኛ ፍልስፍና እንዳይታወቅ  ማዕቀብ ተደርጎብናል? ችግሩ ከእኛ ከሆነስ፣ ለምን ፍልስፍናችንን ለቀረው ዓለም ለማሳወቅ ዳተኛ ሆንን? እስቲ መልስ አምጡ!

 የአውቶሞቲቭ ኢንዱስትሪው የደረሰበት እመርታ አንዱ መገለጫ እንደሆነ ሲነገርለት የነበረው አዲሱ ሾፌር አልባ አውቶብስ፤ በአሜሪካ ላስቬጋስ ውስጥ 15 መንገደኞችን አሳፍሮ የመጀመሪያውን የሙከራ ጉዞ በጀመረ በሰዓታት ጊዜ ውስጥ በአቅራቢያው በቀስታ ሲጓዝ ከነበረ የባለሾፌር የጭነት መኪና ጋር መጋጨቱ ተነግሯል፡፡
በአሜሪካ ታሪክ ለመጀመሪያ ጊዜ መኪኖች በሚንቀሳቀሱበት ጎዳን ላይ የሙከራ ጉዞ በማድረግ የመጀመሪያው ነው የተባለውና ናቪያ የተባለው ታዋቂ የፈረንሳይ የአውቶሞቲቭ ኩባንያ የምርምር ውጤት የሆነው ይህ ሾፌር አልባ አውቶቡስ፤ በድንቅ ፈጠራነቱ በመገናኛ ብዙሃን ተወድሶ ሳያበቃ፣ በሰዓት 25 ኪሎ ሜትር ፍጥነት በመጓዝ ላይ እያለ ግጭቱ እንደደረሰበት ቢቢሲ ዘግቧል፡፡ ምንም እንኳን ክስተቱ የብዙዎችን ትኩረት ቢስብም፣ አደጋው ቀላል ግጭት እንደሆነና በተሳፋሪዎች ላይ ምንም አይነት ጉዳት አለመድረሱን የላስ ቬጋስ ከተማ ቃል አቀባይ መናገራቸውን ዘገባው አመልክቷል፡፡
ትኩረት ያገኘው ሾፌር አልባው አውቶቡስ ቢሆንም፣ በወቅቱ በአካባቢው የነበሩ የትራፊክ ፖሊሶች ግን፣ “ሾፈር አልባው አውቶብስ በአግባቡ እየተጓዘ እያለ አቅጣጫውን ስቶ አደጋውን ያስከተለው ባለሾፌሩ የጭነት መኪና ነው” ሲሉ ለሾፌሩ የቅጣት ወረቀት መቁረጣቸውንም ዘገባው አክሎ ገልጧል፡፡

 የኮሎምቢያ ፖሊስ በህገወጥ መንገድ ወደ አሜሪካ ሊላክ ተዘጋጅቶ የነበረ 12 ሺህ ኪሎ ግራም ኮኬይን የተባለ አደንዛዥ ዕጽ በቁጥጥር ስር ማዋሉን ያስታወቀ ሲሆን ግምቱ 360 ሚሊዮን ዶላር ያህል እንደሆነም ተነግሯል፡፡
ይህን ያህል ክብደት ያለው አደንዛዥ ዕጽ በአንድ ጊዜ በፖሊስ ቁጥጥር ስር ሲውል ይህ በአገሪቱ ታሪክ የመጀመሪያው ነው ያለው ቢቢሲ፤ የአደንዛዥ ዕጹ ባለቤትም ገልፍ ክላን የተባለው እጅግ አደገኛ የወንጀለኞች ቡድን ፊታውራሪ ዳሪዮ ኡሳጋ የተባለ ግለሰብ መሆኑን  ጠቁሟል፡፡
የአገሪቱ ፖሊስ ቀንደኛውን ወንጀለኛ ዳሪዮ ኡሳግን ለመያዝ ለአመታት ደፋ ቀና ቢልም አሁንም ድረስ እንዳልተሳካለት የጠቆመው ዘገባው፤ ፖሊስ ይህንኑ ቡድን ለመቆጣጠር በጀመረው ዘመቻ፣ ዕጹ በአገሪቱ ሰሜናዊ ግዛት በአንድ የሙዝ እርሻ ውስጥ ተደብቆ ማግኘቱን አመልክቷል፡፡
የሽብር ቡድኑ አባላት የሆኑ ከ1 ሺህ 500 በላይ ግለሰቦችን በቁጥጥር ስር ያዋለው የአገሪቱ ፖሊስ፤ ከአደንዛዥ ዕጹ ጋር ንክኪ አላቸው ያላቸውን የቡድኑ ግብረአበሮች የሆኑ አራት ግለሰቦችን መያዙን የጠቆመው ዘገባው፤ ባለፉት ሁለት ወራት ብቻ በአገሪቱ የተለያዩ ክፍሎች 20 ቶን ያህል አደንዛዥ ዕጽ መያዙንም አስታውሷል፡፡

  የዚምባቡዌን መሪ የጤና አምባሳደር አድርጎ በመምረጡ ዓለማቀፍ ውግዘት የገጠመውና የሾማቸውን ሙጋቤን ባፋጣኝ ከሻረ አንድ ወር ያልሞላው የዓለም የጤና ድርጅት፤ ቡና፣ ሞባይልና የታሸጉ የስጋ ምርቶች ለካንሰር በሽታ ያገልጣሉ የሚል ሃሰተኛ የጥናት ውጤት ይፋ አድርጓል በሚል አዲስ ውንጀላ ቀርቦበታል፡፡
ሮይተርስ የዜና ወኪል የዓለም የጤና ድርጅት በቅርቡ ይፋ ባደረገው ካንሰርን የተመለከተ የጥናት ውጤት ላይ ባደረገው ጥልቅ ምርመራ፣ ጥናቱ ከመውጣቱ በፊት በነበረው ሰነድ ላይ ቡና፣ ሞባይልና የታሸጉ የስጋ ምርቶች ለካንሰር በሽታ ስለማጋለጣቸው ምንም አይነት ነገር አለመጠቀሱን ጠቁሞ፣ ድርጅቱ ባወጣው የመጨረሻ ይፋዊ ሰነድ ላይ ግን ለካንሰር ያጋልጣሉ ብሎ  አዛብቶ ማውጣቱን  ማረጋገጡን አስታውቋል፡፡
ይህን ተከትሎም ሁለት የአሜሪካ የኮንግረስ አባላት የአለም የጤና ድርጅት ቡና መጠጣት፣ ሞባይል መጠቀምና የታሸጉ የስጋ ምግቦችን መጠቀም ለካንሰር ስለማጋለጣቸው ተጨባጭ ማስረጃውን ይስጠን ሲሉ መጠየቃቸውን የጠቆመው ዘገባው፤ ጉዳዩ በተቋሙ ተሰሚነት ላይ ከፍተኛ ተጽዕኖ ሊፈጥር ይችላል መባሉን አክሎ ገልጧል፡፡

 በአሜሪካ መንግስት አደንና ክትትል ከ6 አመታት በፊት በፓኪስታኑ አቡታባድ የተገደለው የአልቃይዳው መሪ የኦሳማ ቢንላደን ልጅ ሃማዝ፤ ጂሃዲስቶች በአሜሪካ ላይ ከፍተኛ የሽብር ጥቃት በመፈጸም የአባቱን ግድያ እንዲበቀሉለት ሰሞኑን ባወጣው የድምጽ መልዕክት ጠይቋል፡፡
ሃማዝ ቢን ላደን፤ “ጂሃዲስቶች በአሜሪካውያን በተለይ ደግሞ አባቴን ለመግደል በተደረገው የግፍ ዘመቻ ተሳታፊ በሆኑት ላይ ሁሉ በቻሉት መንገድ የሽብር ጥቃት በመፈጸም እንዲበቀሉልኝ እጠይቃለሁ” ሲል በአልቃይዳ የፕሮፓጋንዳ ማሰራጫዎች በኩል ባስተላለፈው መልዕክት መናገሩን ዘ ኢንዲፔንደንት ዘግቧል፡፡
“አባቴ የጂሃድን መንፈስ የቀየረ ጀግና ሰማዕት ነው” በማለት ቢን ላደንን ያወደሰው የ28 ዓመቱ ሃማዝ፤ 25 ደቂቃ ያህል እርዝመት ባለው የድምጽ መልዕክቱ፣ የአፍጋኒስታኑን ታሊባን ቢያደንቅም አይሲስን በተመለከተ ግን ምንም ነገር አለማለቱን ዘገባው አመልክቷል፡፡
አሜሪካ በ2011 ቢን ላደንን በገደለችበት ወቅት የሃማዝ ወንድም ካሊድ መገደሉን ያስታወሰው ዘገባው፤ የአሜሪካው የስለላ ተቋም ሲአይኤ ባለፈው ሳምንት ከዚህ በፊት ታይተው የማይታወቁ ከቢን ላደን ጋር ተያያዥነት ያላቸውን በርካታ መረጃዎች ይፋ ማድረጉንም አስታውሷል፡፡

 ከዕለታት አንድ ቀን አንድ እጅግ የሚያምር ልጅ፤ ከአሸዋ ላይ አንዲት ትንሽ ጉድጓድ ቆፍሮ፣ እዚያች ውስጥ ከባሕሩ ውሃ በትንሽ ዛጎል ሳያቋርጥ ቶሎ ቶሎ እያመላለሰ ይጨምር ነበር፡፡ ውሃውን ለማቆር እየሞከረ ነው ማለት ነው፡፡
አንድ የተማረና የተመራመረ በጣም የረቀቀ ቅዱስ፤ ያንን ልጅ ባየ ጊዜ ሀሳቡ ተሳበ። ወደ ልጁ ቀረበና፤
“አንተ ልጅ ምን እያደረግህ ነው? እዚች ትንሽዬ ጉድጓድ ውስጥ ውሃ ለመጨመር ይህን ያህል አዕምሮህ እስቲጠፋ ድረስ የምትደክመው ለምንድን ነው?” ሲል ጠየቀው።
ልጁም፤
“ባህሩን አጠንፍፌ ውሃውን ሁሉ እዚህ ጉድጓድ ውስጥ ለመጨመር እፈልጋለሁ” ሲል መለሰለት፡፡
ቅዱሱም፤
“ያንን ለማድረግ ፈፅሞ አይቻልም፡፡ ባሕሩ ምን ያህል ትልቅና ሰፊ መሆኑንና እንደዚች ባለች ትንሽ ቀዳዳ ውስጥ ይህንን ስፍርና ልክ የሌለውን ውሃ ለማግባት እንደምን እችላለሁ ብለህ ታስባለህ? የማይቻልን ነገር ለማድረግ መሞከርስ ትርፉ ድካም መሆኑን መገንዘብ እንዴት ያቅትሃል?” አለው ቅዱሱ ሰው፡፡
ልጁም፤ እጅግ የረቀቀ ትርጉም ባለው አስተያየት ትኩር ብሎ ተመለከተውና ወዲያው፤
“እኔ ባሕሩን ለማጠንፈፍና ከዚች ጉድጓድ ውስጥ መክተት ዕውን አልችልምን? ለምን ሙከራዬን ታናንቅብኛለህ? አንተ ከባሕሩ ሚሊዮን ጊዜ የሚበልጠውን የሥላሴዎችን ምስጢርና ባሕሪያቸውን ለማወቅ ትፈልግ የለምን? እዚህ አሸዋ ላይ ካደረግኋት ከትንሿ ጉድጓድ ይልቅ ወሰን ከሌለውና ይህ ይቀረዋል ከማይባለው የአምላክ ዕውቀት፤ በጣም ያነሰውን ናላህ ውስጥ አኑረህ ለመሸከም ጥረት ታደርግ የለምን?” ሲል ጥያቄያዊ ምላሽ አቀረበለት፡፡ ከዚያም ልጁ የሰማይ ብርሃን ተጎናፅፎ ወዲያው ተሰወረ፡፡ ይህ ህፃን የአምላክን ትልቅ መልዕክት ለቅዱሱ ሊናገር የተላከ ነበር ይባላል!
*       *      *
ትልቁ ነገር የሀገርን ትልቅ ስዕል ማየት ነው! ምንጊዜም ትናንሽ ችግሮች ይኖሩብናል። ልንፈታቸው የሚገባን ግን ትልቁን የሀገር ስዕል ካስተዋልን ነው! አያሌ መንገዶች ወደ መፍትሔ ሊመሩን ይችላሉ፡፡ ከመንገዶች ሁሉ የተሻለውን ለመምረጥ ግን ልዩ ዕይታን ይጠይቃል፡፡ ትልቁ ቁምነገር ጥመትን አስቀድሞ ከላይ ማስወገድ ነው፡፡ ብላቴን ጌታ ማህተመ ሥላሴ ወ/መስቀል እንዲህ ይሉናል፡-
“ምንም ወፍጮ መፍጨት፣ ውሃ መቅዳት፣ እንጀራና ዳቦ መጋገር፣ ወጥ መስራት፣ ለሴት የተለመደ የዘወትር ተግባሯ ቢሆንም፤ ማታ ማታ ባሏን እራት ካበላች በኋላ ጥጧን አቅርባ በእሳት ዳር ሆና ትፈትላለች፤ በቡልጋ ድርና ማጉን ፈትሎ እዚያው በሚገኘው ሸማኔ አሰርቶ ለቤተሰብ አስፈላጊ የሆነውን ልብስ ማዘጋጀት የተለየ የሴቶች ባልትና ነው፡፡ በዚህም ጊዜ እንዲህ ስትል ታንጎራጉራለች፡-
“ባሰላው ባሰላው እንቢ አለኝ እንዝርቱ
 ከታችም አይደለ ከላይ ነው ጥመቱ”
ጥመቱ ከላይ ሲሆን፣ ብልሽቱ ከላይ ሲመጣ፣ አደጋው የትየለሌ ነው፡፡ ታች ድረስ ይሰማል፡፡ ይናጋል፡፡ የሥርዓት መናድ ያስከትላል፡፡ ይህን ሁኔታ ለማስተካከል ጊዜ፣ የሰው ኃይልና አንጡራ - ሀብት መውጣት ይኖርበታልና የሚያስከፍለው ዋጋ ከባድ ነው! አያሌ ችግሮች አሉብን- የላይኛው መዋቅር መዛባት፣ የፍትሕ መዛባት፣ የዲሞክራሲ መቃወስ፣ የሀብት ክፍፍል መላ - ቅጥ መጥፋት፣ የገዢና ተገዢነን አግባብ ማጣት፣ የነባራዊ ሁኔታና የህሊናዊ ሁኔታ አለመጣጣም- ወዘተ… የሥርዓት መናጋት ሥራዬ ብሎ አለማጤን፤ ለሁሉም ወገን አለመረጋጋት ይዳርጋል፡፡ ከሁሉ በላይ የሥልጣን ገዋ (Power vacuum) ቢፈጠርስ ማለትም ደግ ነው! ጉዳዮችን በመልክ በመልካቸው ሰድሮ ለማየት ቅንነትና ከተንኮል - የፀዱ መሆንን ይጠይቃል፡፡ ሆኖም ቀናት ብቻውን፣ ያለ ፖለቲካ ብስለት የትም አያደርስም፡፡ ምክንያቱም ቀናነት ወደፈለጉት አቅጣጫ አጣመው ለራሳቸው ጥቅም የሚያውሉ እኩያን ሊኖሩ ይችላሉ!
የይስሙላ ፍቅር፣ የይስሙላ አጋርነት፣ የይስሙላ ጓድነት እጅግ ጊዜያዊ ዕድሜ ያለው፤ “ላያዘልቅ ፀሎት ለቅስፈት” የሚባለውን አይነት ነው፡፡ ለወጉ “ዘላቂነት ዘላቂነት” ብንል …መንግሥታዊ ያልሆኑ ድርጅቶች መፈክር ከመሆን አያልፍም፡፡ ያለንበት የሚመስለን ኳስ ጨዋታ ለተለዋጭነት (ለቤንችነትም) የማያበቃን ሆኖ ሊገኝ ይችላል፡፡ “የት ይደርሳል የተባለው ባህር ዛፍ ቀበሌ ቆረጠው፡፡” ከመባል አያልፍም። ነኝ የምንለውን ነገር፣ በእርግጥ ነን ወይ? ብሎ መጠየቅ ያባት ነው፡፡ በፖለቲካ ትግል ውስጥ ፈጣን ተለዋዋጭ ሁኔታ (Volatility) ያለ ነገር ነውና እርግጠኝነት ወደ ፍፁምነት አድጓል ብሎ መፈጠም የዋህነትም፣ አዳጋችም ነው፡፡ “ገንፎ እፍ እፍ ቢሉሽ ሊውጡሽ” ነው፤ ዕውነት አይምሰልሽ!” የተባለው ተረት ቁም ነገሩ ይኸው ነው!

• *ለኪራይ ሰብሳቢነት የተመቸውን ፖለቲካል ኢኮኖሚ ለመቀየር ተስማምተናል
• *የህዝቡ ፍላጎት የደረሰበትን ደረጃ የሚመጥን ድርጅታዊ ቁመና ያስፈልጋል
• *የአንድም ሰው ህይወት መጥፋት የለበትም የሚል መግባባት ላይ ደርሰናል

    ኦህዴድ፤ ስለ ኢትዮጵያ አንድነትና ስለ ህብረ ብሄራዊ ፌደራሊዝም የሚያስቡ የቀጣይ ትውልድ አመራሮችን በስፋት ለማፍራት አቅጣጫ ማስቀመጡን አስታወቀ፡፡ 2 ሺህ ያህል ተሳታፊዎች በታደሙበት የአዳማ ገልማ አባ ገዳ አዳራሽ፣ ከጥቅምት 19 እስከ 23 ቀን 2010 ዓ.ም በተደረገው የኦህዴድ 7ኛው ድርጅታዊ ኮንፈረንስ ላይ፤ ስለ ክልሉ የፀጥታ ጉዳይ፣ ከኢትዮጵያ ሶማሌ ክልል
ጋር ስላጋጠመው ችግር፣ ስለ ፌደራሊዝምና ስለ ኢትዮጵያ አንድነት ጉዳይ በስፋት ውይይት መካሄዱን የክልሉ የኮሚኒኬሽን ጉዳዮች ኃላፊና የኮንፈረንሱ ቃል አቀባይ አቶ አዲሱ አረጋ ለአዲስ አድማስ ጠቁመዋል፡፡  ከህብረ ብሄራዊ ፌደራል ሥርአት ግንባታ ጋር በተያያዘ  ሰፋ ያለ ሃሳብ መንሸራሸሩንና ለሀገሪቱ ከህብረ ብሄራዊ ፌደራላዊ ሥርአት ውጪ ሌላ አማራጭ እንደሌለ በመተማመን፣ ኦህዴድና የክልሉ ህዝብ ፌደራሊዝምን በመገንባት ረገድ ወሳኝ ሚና እንዳላቸው መግባባት ላይ መደረሱን ቃል አቀባዩ አስታውቀዋል፡፡ በፌደራል ሥርአቱ ግንባታ ውስጥ በርካታ ተግዳሮቶች እያጋጠሙ መሆኑን የገመገመው ኮንፈረንሱ፤ ይህንንም ከኢህአዴግ አባል ድርጅቶችና አጋሮች ጋር በመሆን በትዕግስትና በዲሞክራሲያዊ መንገድ መፍታት እንደሚገባ አቅጣጫ አስቀምጧል ብለዋል - አቶ አዲሱ፡፡ የኢትዮጵያ አንድነትንና የህብረ ብሄራዊ ፌደራሊዝምን ከማጠናከር አኳያም “የተሃድሶው የኦህዴድ አመራሮች” ትልቅ ድርሻ አለን ያሉት ቃል አቀባዩ፤ “የሀገራችንን የኢትዮጵያን አንድነት ከማጠናከር አንፃር ሚናችን ጉልህ ስለሆነ፣ያንን ሚናችንን መወጣት አለብን የሚል አቅጣጫ ተቀምጧል” ብለዋል፡፡ ስለ ኢትዮጵያ አንድነት፣ ስለ ህብረ ብሄራዊ ፌደራል ሥርአት፣ ስለ ህዝቦች ወንድማማችነት የሚያስብና ከምንም በላይ ለሀገርና ለዜጎች የሚቆም የቀጣይ ትውልድ አመራር በኦህዴድ በኩል የመፍጠር ስራ እንዲሰራም መታቀዱን አቶ አዲሱ ለአዲስ አድማስ አብራርተዋል፡፡ “ኦሮሞ ሲጠቀም አማራው፣ ትግሬው ወላይታው -- ይጠቀማል” የሚል አስተሳሰብ በመያዝ፣ ለህዝቦች መቀራረብና የሀገር አንድነትን ለማምጣት ግልፅ መግባባት ላይ መደረሱንም ቃል አቀባዩ አስረድተዋል፡፡የህዝቡን ፖለቲካዊ፣ ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ ችግሮች ለመፍታት፣ የህዝቡ ፍላጎት የደረሰበትን ደረጃ የሚመጥን ድርጅታዊ ቁመና ያስፈልጋል በሚል መግባባትም፤ በቀጣይ ከቀበሌ ጀምሮ እስከ ላይኛው የኦህዴድ ድርጅታዊ መዋቅር ድረስ እንደገና የማጠናከር ሥራ እንዲሰራም ታቅዷል ተብሏል፡፡  “በህገ መንግስቱ የተቀመጡ መብቶች ሳይሸራረፉ፣ ሙሉ ለሙሉ እንዲተገበሩ ሚናችንን ለመወጣትም ተስማምተናል” ያሉት ቃል አቀባዩ፤ የፍትሃዊ ኢኮኖሚ ተጠቃሚነትን በተመለከተም በክልሉ ነዋሪ የሆኑ ሁሉም ዜጎች፣ የኢኮኖሚ አብዮቱ ተሳታፊና ተጠቃሚ እንዲሆኑም አቅጣጫ መቀመጡን ገልጸዋል፡፡ “ከመልካም አስተዳደር አኳያ፣ ከአገልግሎት አሰጣጥ፣ ከፍትህ ሥርአቱና ከፕሮጀክቶች መጓተት ጋር ተያይዞ ብዙ ያልተሻገርናቸው ችግሮች እንዳሉ ተገምግሟል፤ በአጠቃላይ ለኪራይ ሰብሳቢነት የተመቸውን ፖለቲካል ኢኮኖሚ
ለመቀየርም መግባባት ላይ ተደርሷል” ብለዋል፤አቶ አዲሱ፡፡ ሌላው የኮንፈረንሱ አጀንዳ  ከፀጥታ ጉዳይ ጋር የተያያዘ እንደነበር ጠቁመው፤ አሁን በክልሉ አንዳንድ አካባቢዎች የሚታየው ግርግር፣ በኪራይ ሰብሳቢዎች ሴራ የተወጠነ መሆኑን መግባባት ላይ ደርሰናል ብለዋል፡፡ “እኛ የክልሉ አመራሮች፤ ከእንግዲህ የአንድም ሰው ህይወት መጥፋት የለበትም የሚል ስምምነት ላይ ደርሰናል” ያሉት ቃል አቀባዩ፤ ”የተፈፀሙ ግድያዎችና የደረሱ ጉዳቶችም በፅኑ ተወግዘዋል” ብለዋል፡፡
በሶማሌ - ኦሮሚያ ግጭት ምክንያት ስለተፈናቀሉ ወገኖች አጥብቆ የተወያየው ኮንፈረንሱ፤ በግጭቱ ምክንያት ፌደራሊዝሙ አደጋ ውስጥ ገብቷል ሊባል እንደማይችልና ችግሩን በሰከነ መንገድ መፍታት እንደሚያስፈልግ አቅጣጫ መቀመጡን አቶ አዲሱ አብራርተዋል፡፡    


   አንዳንድ ዕውነተኛ ታሪክ ሲቆይ ተረት ይመስላል፡፡ ከዕለታት አንድ ቀን አንድ ትልቅ ቴያትር ቤት ፊት ለፊት አንድ ወጣትና አንዲት ወጣት ቆመዋል፡፡ የቆሙበት ቦታ የቴያትር ቤቱ ኮሪደር ነው፡፡ ሰው ቴያትር ለመግባት የሚሠለፈው እዚሁ ኮሪደር ላይ ነው፡፡ ስለዚህ ሰው እየመጣ ከወጣቱና ከወጣቷ ጀርባ መሰለፍ ጀመረ፡፡ ቀስ በቀስ ሰልፉ በጣም እየረዘመ ወደ ዋናው የግቢው በር እየደረሰ ሄደ፡፡
የቴያትሩ መጀመሪያ ሰዓት ደርሶ ተዋንያኑ መልበሻ ክፍል ገብተው ተዘጋጅተዋል፡፡ ሰው ግን ትኬት እየቆረጠ አይደለም፡፡ የቴያትር ቤቱ ዳይሬክተር ግራ ገብቶታል፡፡ ሲጃራውን በላይ በላዩ እየለኮሰ ያጨሳል፡፡ ወደትኬት መቁረጫው ክፍል መጥቶ፤
“ለምንድን ነው ሰው ማስገባት ያልጀመራችሁት?” ሲል ጠየቀ፡፡
ትኬት ቆራጯ፤
“ኧረ እኛ ዝግጁ ነን፡፡ ሰው ግን ወደ እኛ አልመጣም፡፡ ለምን እንደማይመጣ አላውቅም!”
ዳይሬክተሩ ወደተሰለፈው ህዝብ ሄዶ፤
“ለምንድን ነው ትኬት ቆርጣችሁ የማትገቡት?” ሲል ጠየቀ፡፡
ከፊት የተሠለፉት ሁለቱ ወጣቶች፤
“ኧረ እኛ አዲስ ፍቅረኛሞች ነን፤ እዚህ ጋ ተቃጥረን ነው!” አሉ፡፡
“ሌሎቻችሁስ” አለ ዳይሬክተሩ፡፡
ሌሎቹ፤
“እኛ እነሱን ዓይነት ነው”
ዳይሬክተሩም፣ ለወጣቶቹ፤
“በሉ እናንተ መንገድ ልቀቁ፤ ሌሎቻችሁ ግቡ”
አስገባቸው፡፡
* * *
የመንገኝነት ችግር የሁልጊዜ ችግራችን ነው፡፡ ሌሎች ሲሰለፉ መሰለፍ፣ ጫማ ቤት ሲከፈት ካየን ጫማ ቤት መክፈት፣ አንዱ ኬክ ቤት ሲከፍት ሌላውም ኬክ ቤት መክፈት ልማዳችን ነው፡፡
ሎሬት ፀጋዬ ገ/መድህን በሼክስፒር ሀምሌት ውስጥ፤
“ዛሬ ለወግ ያደረግሺው፣
ወይ ለነገ ይለምድብሻል፤
ልማድ ፊት እንዳሳዩት ነው፣
ወይ ይጠፋል፣ ወይ ያጠፋል
ከርሞም የሠለጠነ እንደሁ፣
ተፈጥሮ ይሆናል ይባላል!”
ይለናል፡፡
የለመድነውን ነገር ለመለወጥ አንችልበትም፡፡ ለለውጥ ሁሌም አዲስ የምንሆነው ለዚህ ነው፡፡ የሚገርመው ለውጥ እንደማይገባን አለመረዳታችን ነው።
“እናውቃለን
ብንናገር እናልቃለን”
… የሚለውን አባባል ዝተን-ዓለማችንን ስንደጋግመው ኖረናል፡፡ እስከ ዛሬም አልለወጥነውም፡፡ ቢሳካልን፤
“እናውቃለን
ባንናገር እናልቃለን”
… ማለትንም ብንማር መልካም ነበር፡፡
“ፊት የተናገረን፤ ሰው ይጠላዋል ፊት የበቀለን፤ ወፍ ይበላዋል” ስንባባል ከርመናል፡፡ ይሄንንም ለመለወጥ ዝግጁ መሆን ይገባናል፡፡ ምነው ቢባል፤ አስቀድሞ ያወቀ አስቀድሞ ማሳወቅ ይገባዋልና! በዘልማድ አንዴ የተዋሀዱንን አባባሎች ተሸክመን መጓዝ የለብንም፡፡ ተገቢ ሆኖ ሲገኝ መለወጥንም መልመድ ቢያንስ ከወግ-አጥባቂነት ያድናል፡፡ ልማዶቻችንን እንፈትሻቸው! ክፉውን ከደጉ እንለይ፡፡ ደጉን ለማዘመን ዝግጁ እንሁን፡፡ የሚተካውን እንተካ! የሚሻሻለውን እናሻሽል- ባለበት-ሀይ እያልን በተለመደው መንገድ ብቻ መዳከሩ መንቀዝን ያስከትላል፡፡ መታደስና መለወጥ እንጂ መንቀዝ ክፉ ልማድ ነው፡፡ Regeneration, not degeneration  እንዲሉ ፈረንጆቹ፡፡ “ልማድ ሲሠለጥን ተፈጥሮ ይሆናል” የሚባለው ለለውጥ ዝግጁ ያልሆነን ህብረተሰብ አመላካች ነው፡፡ ለውጥ የእፎይታን ያህል ነው ይላሉ፤ የፖለቲካ ጠበብት፡፡ “a change is as equal to rest” ብለው ቀድሞ ጠቁመውናል! ዐይናችንን እንከፈት፡፡

Sunday, 05 November 2017 00:00

ከፌስ ቡክ ገፅ

 
             የምሁራን ሚና ምንድን ነው?

        እንደ ጣና ተለቅ እና ጠለቅ፣ እንደ ዓባይም ረዘም ያለ ዓላማ/አጀንዳ የሚኖረው ጉዞ......

   ኦቦ ለማ መገርሳ ከነገ ወዲያ ቅዳሜ ከፊንፊኔ ይነሱና ወደ ዓባይና ጣና መገኛ... ወደ አማራ ክልል... ወደ ባሕር ዳር ይሄዳሉ። ጉዞው የፍቅርና የምክር ነው። የሰላም ጉዞ !
የኦሮሚያው ፕሬዝዳንት ለማ መገርሳ የብቻቸውን አይደለም ወደ አማራ የሚያቀኑት። ከ 300 በላይ የኦሮሚያ ባለሥልጣናት፣ የሀገር ሽማግሌዎች፣ ባለሀብቶች እና የዲያስፖራ አባላትም አብረዋቸው ይጓዛሉ። ከአማራ ክልል አቻዎቻቸው ጋርም በልዩ ልዩ ጉዳዮች ላይ ይመክራሉ። እግረ መግዳቸውንም የተለያዩ የቱሪስት መዳረሻዎችን ይጎበኛሉ። ከጣና የገነትን ንጹህ አየር እየሳቡ በባሕር ዳር ዘንባባዎች ሰልፍ ታጅበው ይዝናናሉ። በባሕር ዳር ውበት ሐሴትን ተላብሰው ጣናን በጥልቀት እያዩ እምቦጭን ይረግሙታል።
የጣናን አፍንጫ ተጠግታ በግዮን እግር ስር ከተቆረቆረችው ውቢቱ ባሕር ዳር ከመድረሳቸው በፊት... ገና ሰላሌን አልፈው ዓባይን ሲሻገሩና የአማራ ክልልን ሲረግጡ... ከደጀን ጀምሮ ልዩ አቀባበል ይጠብቃቸዋል። አቀባበሉ በሰዎች ብቻ ሳይሆን በተፈጥሮም ይታጀባል። አሁን ጥቅምት እያለቀ ነው። የጎጃም ምድር ሰብልን አዝሎ አሽቷል። የደጀን ለጥ ያለ ሜዳ በንፋስ አቅጣጫ በሚዘናፈል ማኛ ጤፍ ተሸፍኖ የመንገዱን ግራና ቀኝ አስውቦታል። በየማሳው ድንበር አደይ አበባ ፈክቷል። ተምጫ ወንዝን ተሻግሮ ምዕራብ ጎጃም ለም መሬት ባሸተ በቆሎ ተሸልሟል። ሳይበሉት ያጠግባል። ለዓይን ይማርካል፤ መንፈስን ያረካል።
የአዊ ሜዳዎች አረንጓዴ ናቸው። በድንች፣ በስንዴና በጤፍ አዝርእት ተሸፍነዋል። ሌላ ውበት.... ሌላ ሐሴት። ይህ የተፈጥሮ ቅኔ ብዙ ጥሪን ያስተላልፋል። በልዩነት ተውቦ አንድ የመሆንን ጥሪ።
የማኛ ጤፍ እንጀራ ምን በባለሙያ ተውቦ ቢጋገር፣ በጋራ መዓድ ካልበሉት አያምርም። መሶብ ሞልቶ በተዘናፈለው የለምለም እንጀራ መዓድ ዙሪያ የበቆሎ ጠላ ተቀድቶ ካልተቀመጠ ስሜትን ምሉዕ አያደርግም። አብሮ መብላት ባህላችን ነው። የሩቅ ወዳጅ ዘመድ ሲኖር ቤት ይደምቃል። አብሮነት ውበታችን ነው። አንድነት የሚያምረው ልዩነት ሲኖር ነው። ልዩነት ከሌለ ስለ አንድነት ማን ያወራል? አንድ የመሆን መንፈስ የሚመነጨው ከልዩነት ነው።
እሁድ ኦቦ ለማና የአማራው አቻቸው አቶ ገዱ አንዳርጋቸው የሚመሩት የጋራ መድረክ ይጠበቃል። ከመድረኩም ብዙ አጀንዳዎች። ከአጀንዳዎችም ብዙ ተስፋዎች።
ከመድረኩ የለማ መገርሳ የአንድነትና የፍቅር ስብከት ይጠበቃል። ሰውዬው ሲናገር ያምርበታል። አንደበቱ ይጣፍጣል። ለነገሩ ፍቅርና አንድነትን የሚሰብክ አንደበት ላይጣፍጥ አይችልም።
የአማራ እና የኦሮሞ የበለጠ መግባባትና መተሳሰር ለሀገራችን ብዙ ማለት ነው። በጣም ብዙ። የሁለቱ ክልሎች ግንኙነት መጠናከር ማለት ከ80 ሚሊዮን በላይ የሚሆነው የሀገራችን ሕዝብ አብሮነት ማለት ነው። የሕዝቦች አብሮነት ሀገርን ከፍ ያደርጋታል።
ሁሉንም የኢትዮጵያን ሕዝቦች በፍቅር አንድ ያድርግልን!!
ሰርገኛ ጤፍ ማን ነው?
(Andualem Y)
አንድ ወቅት ላይ የኦሮሞ ባላባቶች አንዲት የኦሮሞ መንግስት ለመመስረት አቅደው እንደነበር ይነገራል፡፡ የሀሳቡ አመንጪና ዋና አቀንቃኝ ደግሞ የጅማው አባ ጅፋር ልጅ ሱልጣን አባ ጆቢር ነበር። አባ ጆቢር ይሄንን እቅዳቸውን ለአካባቢ ባላባቶች ባማከሩ ጊዜ፣ ከባላባቶቹ መካከል ከአንዱ፣ የሜጫና ጅባት ባላባት ከሆኑት ከአባ ዶዮ ከባድ ፈተና ገጠማቸው፡፡
አባ ዶዮ፣ ቀይና ነጭ ጤፍ ደባልቀው “እስክመለስ ድረስ ለዩና ጠብቁኝ” ብለው ሄዱ። ሲመለሱ ጤፉን መለየቱ የማይቻል መሆኑ ሲነገራቸው፣ “በሉ አማራንና ኦሮሞን ለመለያየት ስለሚያስቸግር አገራችንን በህብረት እንገንባ እንጂ መለያየቱ ይቅር” አሉና ዕቅዱ ሥራ ላይ ሳይውል ቀረ፣ እየተባለ በሰፊው ይወሳል፡፡ (የ20ኛው ክ/ዘ/ን ኢትዮጵያ መፅሀፍ ላይ የተወሰደ)
የወቅቱ የኦሮሚያ አስተዳደር፣ እኒያን ብልህ የኦሮሞ መሪ አባ ዶዮን ያስታውሱናል፡፡ አገር ግንባታ ላይ የብቻ ጉዞ እንደማያዋጣ ፅኑ እምነት ይዘው ሲንቀሳቀሱ ማየት ከጀመርን እነሆ አመት ሊሞላን ነው፡፡ በኦቦ ለማ መገርሳ እና ዶ/ር አብይ አህመድ፣ በእኒህ ሁለቱ መሪዎች አንደበት “ኢትዮጵያ” ስትጠራ መስማት ልብን በሀሴት ይሞላል፡፡ በየመድረኩ፣ “ስለ ጠባብነትና ስለ ትምክህት” እየተናገሩ ጆሯችንን አያደሙትም… ይልቁኑ “ስለ አንድነትና ስለ ፍቅር” ደጋግመው ሲናገሩ፣ ስለ ነገ ተስፋ እንድንሰንቅ ያደርጉናል፡፡
አቶ ለማ፣ “የኢትዮጵያ ህዝቦችን ያስተሳሰረው የደም ሐረግ ብርቱ ነው። ድልድያችን ሻማ፣ ከዘራችን ቄጤማ አይደለም፤ ዘመን ባስቆጠረ አብሮነታችን ወደላቀ ደረጃ እንደምንሸጋገር እናምናለን” ይሉናል። በተመሳሳይ፣ ባለፉት ሁለት አስርት አመታት ኢህአዴግ ለፖለቲካ ትርፋ ሲል እርስ በራሱ እንዲጠራጠርና በአይነቁራኛ እንዲተያይ ያደረጉትን የአማራና የኦሮሞ ህዝብ “ላይለያዩ በደም የተገመዱ ህዝቦች ናቸው” ሲሉ ዶክተሩ አብይ አህመድ አስረግጠው ይነግሩናል፡፡
ስለ ልዩነት ሳይሆን ስለ አንድነት፣ ስለ ጥላቻ ሳይሆን ስለ ፍቅር ሲነገር የሚጠላ እሱ ሰይጣን ብቻ ነው፡፡ እኝህ ሁለት የወቅቱ መሪዎች ስለ ፍቅር ሲናገሩ፣ በሚመሩት የኦሮሞ ህዝብ ዘንድ ብቻ ሳይሆን በሌሎች ህዝቦች ልብ ውስጥም እንዲነግሱ አድርጓል፡፡ በሶማሌና በኦሮሚያ ክልል መካከል በተፈጠረውና ለግማሽ ሚሊዮን ሕዝብ መፈናቀል ምክንያት በሆነው ቀውስ ዙሪያ፣ ዶ/ር አብይ ሃረርጌን እንደ ምሳሌ በመጥቀስ ስለ ፍቅር ሲናገሩ፡
“ሐረርጌ የፍቅር ሀገር ናት። ፍቅር ከዚህ ኤክስፖርት ሊደረግ ይገባል። ዓለምና ኢትዮጵያ በፍቅር እጦት በሚሰቃዩበት በዚህ ጊዜ እናንተ ፍቅርን የማታካፍሉን ከሆነ እየበላን እንራባለን…” ነበር ያሉን።
ስለ ኢትዮጵያና ስለ ልጆቿ በአንደበታቸው መልካም የሚናገሩ የፍቅር ሰባኪዎችን ሁሉ የኢትዮጵያ አምላክ ይከተላቸው!!”
ምንጭ//Andualem Y.//
በተለያዩ የሀገሪቱ አካባቢዎች የሕዝብ ተቃውሞና አመፅ እየታየ ነው። በሕዝቡ የተቃውሞ እንቅስቃሴና መንግስት እየወሰደ ካለው እርምጃ አንፃር የሀገሪቱ ምሁራን አቋምና ተግባር ምን መሆን አለበት? በዚህ ረገድ ምሁራኑ ሁለት አማራጮች አሏቸው። አንደኛ፡- የመንግስትን አቋምና እርምጃ በመደገፍ የህዝቡን እንቅስቃሴ ማውገዝ፣ ሁለተኛ፡- ከሕዝቡ ጋር በመሆን የመንግስትን አቋምና እርምጃ መቃወምና መተቸት። ነገር ግን፣ አብዛኞቹ የሀገራችን ምሁራን፣ አንዱን ወገን በመደገፍ ወይም በመቃወም ሃሳብና አስተያየት ሲሰጡ አይስተዋልም። በእርግጥ ምሁራኑ ሃሳብና አስተያየታቸውን በነፃነት እንዳይገልጹ ያደረጋቸው ፍርሃት ነው። ይህ ግን የሚሸሹትን ነገር ከቤታቸው ድረስ መልሶ ያመጣዋል። ከራሳቸው አልፎ፣ በማህበረሰባቸውና በሀገራቸው ላይ ውድቀትና ጭቆና እንዲነግስ ያደርጋል።
በዘንድሮ አመት የተነሳውን የተቃውሞ አንቅስቃሴ ለመግለፅ በስፋት ጥቅም ላይ ከዋሉ ቃላት ውስጥ፤ “ሰላም – ፀረ-ሰላም፥ ሽብር – ፀረ-ሽብር፥ ልማት – ፀረ-ልማት፥ ሕዝብ – ፀረ-ሕዝብ፥ ሕጋዊ – ሕገ-ወጥ፣..” የመሳሰሉት የሚጠቀሱ ናቸው። በተለይ ደግሞ በመንግስት ሚዲያዎች፤ “የፀረ-ሰላም ኃይሎች፥ የነውጥና ብጥብጥ ቀስቃሾች፥ የሽብር ኃይሎች፥…” የሚሉ ለዛ-ቢስ አባባሎች (Cliches)፣ “ሣይቃጠል በቅጠል፥ ፀጉረ-ልውጥ፥…” የመሳሰሉ አሰልቺ ዘይቤዎች (tired metaphors)፣ እንዲሁም “ጥቂት፥ የተወሰኑ፥ አንዳንድ፥…” የሚሉ የግብር-ይውጣ አገላለፆች (lazy writing) በስፋት ይደመጣሉ። እንግሊዛዊው ፀኃፊ ጆርጅ ኦርዌል፤ ይሄን “የፖለቲካ ቋንቋ” በማለት ይገልፀዋል። የሀገራችን ምሁራን በፖለቲካዊ ጉዳዮች ላይ ሃሳብና አስተያየታቸውን በነፃነት እንዳይገልጹ ያደረጋቸው ፍርሃት ዋና ምንጩ ደግሞ የፖለቲካ ቋንቋ ነው።
የፖለቲካ ቋንቋ በስፋት በሚዘወተርበት ሁኔታ አብዛኞቹ ምሁራን “ደጋፊ” ወይም “ተቃዋሚ” ተብለው በጅምላ እንዳይፈረጁ በመስጋት አስተያየት ከመስጠት ይቆጠባሉ። እንደ ኢትዮጵያ ባሉ ሀገራት ደግሞ ሃሳብን በነፃነት መግለፅ፣ ከትችትና ነቀፌታ አልፎ ለእስራትና ሞት ሊዳርግ ይችላል። ስለዚህ ምሁራን በወቅታዊ ጉዳዮች ላይ ሃሳብና አስተያየት በነፃነት መግለፅ ይፈራሉ። ነገር ግን፣ ጆርጅ ኦርዌል፤ የመንግስትን አቋምና እርምጃ በይፋ ለመቃወም የሚፈሩ ምሁራንን “un-political’ imaginative writers” በማለት ይገልፃቸዋል። እነዚህ ምሁራን ለዛ-ቢስ፥ አሰልቺና የግብር-ይውጣ የሆኑ የፖለቲካ ቃላትና አባባሎችን ከሚፅፉትና ከሚያነቡት የመንግስት ጋዜጠኞች ብዙም የተለዩ እንዳልሆኑ እንደሚከተለው ይገልፃል፡-
“And so far as freedom of expression is concerned, there is not much difference between a mere journalist and the most ‘un-political’ imaginative writer. The journalist is unfree, and is conscious of un-freedom, when he is forced to write lies or suppress what seems to him important news: the imaginative writer is un-free when he has to falsify his subjective feelings, which from his point of view are facts. …If he is forced to do so, the only result is that his creative faculties dry up. Nor can he solve the problem by keeping away from controversial topics. There is no such thing as genuinely non-political literature.” (George Orwell, Politics And The English Language, 1946)
በፍርሃት ምክንያት ሃሳብና ተቃውሞን በይፋ አለመግለፅ፣ መንግስት በህዝቡ ላይ እያደረሰ ላለው ጭቆናና በደል፣ ድጋፍና ትብብር እንደማድረግ ነው። ስለዚህ፣ እያንዳንዱ ምሁር ለበደልና ጭቆና ድጋፉን ከመስጠት ይልቅ ፍርሃቱን መጋፈጥ ይኖርበታል። ለዚህ ደግሞ የፍርሃቱ ምንጭ የሆነው የፖለቲካ ቋንቋ፤ መሰረታዊ ዓላማ ምን እንደሆነ ከመረዳት ይጀምራል። እንደ ጆርጅ ኦርዌል አገላለፅ፣ የፖለቲካ ቋንቋ ውሸትን እውነት፣ ግድያን ክብር በማድረግና ከነጭ-ውሸት ጋር ህብረት እንዳለን ለማስመሰል የተቀረፀ ነው “Political language is designed to make lies sound truthful and murder respectable, and to give an appearance of solidity to pure wind”.
በዚህ ላይ ኢድዋርድ ሳይድ የተባለው ምሁር ደግሞ ምሁራን ከእንዲህ ያለ ቋንቋና ተግባር ጋር ምንም ዓይነት ሕብረት ሊኖራቸው እንደማይገባ ይጠቅሳል። እ.ኤ.አ በ1993 ዓ.ም “Representations of an Intellectual – Holding Nations and Traditions at Bay” በሚል ርዕስ በሰጠው ትንታኔ፣ ምሁራን ከተጨቆኑ ወገኖች ጎን በመቆም ትችትና ተቃውሟቸውን የማሰማት ኃላፊነትና ግዴታ እንዳለባቸው እንዲህ ሲል ገልፆታል፡-  “Never solidarity before criticism” is the short answer. …This does not mean opposition for opposition’s sake. But it does mean asking questions, making distinctions, restoring to memory all those things that tend to be overlooked or walked past in the rush to collective judgment and action.”
እንደ ኢድዋርድ ሳይድ አገላለፅ፣ የምሁራን ድርሻና ኃላፊነት መንግስትን በግልፅ መተቸት ነው። ከምሁራን የሚጠበቀው፣ ሁሉንም ነገር በጭፍን መቃወም ብቻ ሳይሆን፣ ትኩረት ሊሰጣቸው የሚገቡ ነገሮችን መለየትና መፍትሄ የሚሹ ነገሮችን መጠቆም፣ ከዚህ በፊት የተከሰቱ ችግሮችን በማስታወስ ዳግም እንዳይከሰቱ ማሳሰብና የመሳሰሉትን በማድረግ፣ ሕዝብ ለሚያነሳቸው ጥያቄዎች ተገቢ ምላሽ እንዲሰጥ ማድረግ ነው። ነገር ግን፣ እንደ ኢትዮጵያ ባሉ የተለያዩ ብሔሮች፣ ሃይማኖቶችና ቋንቋዎች ባላቸው ሀገራት ነገሮች ቀላልና ቀጥተኛ አይደሉም። አሁን በኢትዮጵያ እንደሚታየው ዓይነት፣ ብሔርና ቋንቋን መሰረት ያደረገ የፖለቲካ እንቅስቃሴ ሲኖር ምሁራን በተዓማኒነታቸው ላይ ምህረት-የለሽ አጣብቂኝ ውስጥ ይወድቃሉ።
እንደ ማንኛውም ሰው፤ ምሁራን የራሳቸው ሀገር፥ ብሔር፣ ማህበረሰብና ቤተሰብ አላቸው። ምንም ዓይነት የፖለቲካ አቋምና አመለካከት ቢኖራቸው፣ ምሁራኑን ከቤተሰቦቻቸው፥ ማህበረሰባቸው፣ ብሔርና ሀገራቸው ጋር ከሚያስተሳስረው ተፈጥሯዊ ገመድ በላይ ጠንካራ ሊሆን አይችልም። በዚህ ምክንያት፣ ለምሳሌ በራሳቸው ብሔር ተወላጆች ወይም በቤተሰቦቻቸው ላይ ጭቆና ሲደርስ ከሌሎች ብሔር ተወላጆች በላይ ሊሰማቸው፣ ከወትሮው በተለየ ትችትና ተቃውሞ ሊያሰሙ ይችላሉ፡፡
በኢትዮጵያ ታሪክ መንግስታት ከአንዱ ወይም ከሌላው ብሔር የቋንቋ፣ ባህልና ሥልጣን የበላይነት ጋር ተያያዥነት አለው። ስለዚህ፣ የመንግስት አስተዳደራዊ ችግሮች በብሔሮች ላይ የተፈፀሙ በደሎችና ጭቆናዎች ተደርገው የመወሰድ እድላቸው የሰፋ ነው። በእንደዚህ ዓይነት ሁኔታ ውስጥ ምሁራን በሕዝቦች መካከል ያለው ልዩነት ሰው-ሰራሽ እንጂ ተፈጥሯዊ እንዳልሆነ ማሳመን ይጠበቅባቸዋል። በአንድ ሕዝብ ላይ የተለየ ጥቃትና ጭቆና ሲደርስ ግን ሕዝቡን በመወከል መተቸትና መቃወም፣ በሕዝባቸው ላይ እየደረሰ ያለውን ወይም ከዚህ በፊት የደረሰውን በደል፣ ጭቆና እና ግድያ በይፋ በመቃወም ለህዝባቸው ያላቸው ድጋፍና አጋርነት መግለፅ ይጠበቅባቸዋል።
ከላይ እንደተገለፀው፣ የምሁራን ኃላፊነት በሀገራቸው፥ ብሔር፥ ማህበረሰብ ወይም ቤተሰብ ላይ የደረሰውን በደልና ጭቆና ከመናገር ባለፈ ተመሣሣይ በደልና ጭቆና በሌሎች ላይ እንዳይደርስ መናገር፣ ማሳወቅ፣ መተቸትና መቃወም ነው። በቀድሞ ስርዓት በእኛ ብሔር፥ ማህበረሰብ ወይም ቤተሰብ ላይ ስለደረሰው ድብደባ፥ እስርና ግድያ መናገርና ማስታወስ እንዳለ ሆኖ፣ የምሁራን መለያ ባህሪ በእነሱ ብሔር፥ ማህበረሰብ ወይም ቤተሰብ ላይ የደረሰው በደልና ጭቆና በሌሎች ላይ እንዳይደገም፣ በእነሱ ላይ ሲደርስ የተቃወሙትን ነገር በሌሎች ላይ እንዳይደርስ መቃወም ነው።
(ከስዩም… ፌስቡክ ተቀንጭቦ የተወሰደ)

እነሆ መፅሀፍ መደብር፣ ሊትማን ቡክስና ክብሩ መፅሀፍት መደብር በመተባበር በየወሩ መጨረሻ ባሉት ቅዳሜና እሁድ የሚያዘጋጁት የመፅሀፍ ሂስ ጉባኤና አውደ ርዕይ የዛሬ ሳምንት ከቀኑ 8፡00 ጀምሮ ጥቁር አንበሳ ት/ቤት ፊት ለፊት በሚገኘው ትራኮን ህንፃ ላይ ይከፈታል፡፡
“ሀሳብን በሀሳብ መፈተን” በሚል መሪ ቃል በሚካሄደው በዚህ የሂስ፤ ጉባኤና አውደ ርዕይ ላይ “የአለቃ ዓፅመ ጊዮርጊስ ገብረ-መሲህ ድርሰቶች (የኦሮሞ ታሪክ ከ1500-1900) የተሰኘው መፅሐፍ ለሂስ የተመረጠ ሲሆን መፅሀፉ በ19ኛው ክ/ዘመን ከተፃፉ መፅሀፍቶች መካከል የአገራችንን የ400 ዓመታት ታሪክና በተለይም የኦሮሞን ህዝብ ታሪክና ባህል በስፋት የሚያስቃኝ ነው ተብሏል  ለሂስና ለውይይት የመነሻ ሀሳብ የሚያቀርቡት በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ የታሪክና ሥነ-ጥበባት መምህር አቶ አበባው አያሌው እንደሆኑም የአውደርዕዩ ዝግጅት አስተባባሪ አቶ በፍቅሩ ዳኛቸው ገልፀዋል፡፡ ቅዳሜና እሁድ አውደርዕዩን የሚጎበኙ የመፅሀፍት እቁብን ጨምሮ ከ25 እስከ 50 በመቶ ቅናሽ የተደረገባቸው መፅሀፍት መግዛት እንደሚችሉ ተጠቁሟል፡፡