Administrator

Administrator

“በፓርቲያችንእንቅስቃሴ ላይ እንቅፋት ይፈጥርብናል”
አቶ አበበ አካሉ
(የ”ሰማያዊ” የውጭ ግንኙነት ኃላፊ)

የፓርቲ ስብሰባ ላይ ሆነን ነው የመረጃ ቋቶቻችንን ከፍተን፣ የአስቸኳይ ጊዜ አዋጁ ለ4 ወራት መራዘሙን ያየነው፡፡ በጣም ነበር ያዘነው፡፡ መንግስት በሀገሪቱ ምንም አይነት ችግር የለም እያለ በሚዲያዎች እየነገረን፣ አዋጁን በድጋሚ ለ4 ወር ማራዘሙ ሀገሪቱ ምን ያህል አስቸጋሪ ሁኔታ ውስጥ እንዳለች ያሳያል፡፡ ሁሉም ነገር ተረጋግቷል፤ሰላም አለ፤በተባለበት ሰአት አዋጁን ማራዘም ለሀገሪቱም አይጠቅምም፤የፖለቲካ ምህዳሩንም ያጠባል፡፡ ለወደፊት የሚታሰሩ ሰዎችም ይኖራሉ ማለት ነው፡፡ እንግዲህ የምናየው ነው የሚሆነው፡፡ ሰላም ሰፍኗል እያሉ አዋጁን የማራዘም ጉዳይ እንዴት እንዳዩት እኛ አናውቅም፡፡ ሰላም ነው ከተባለ ማራዘሙ ተገቢ አይደለም፡፡
የአዋጁ መራዘም በፓርቲያችን እንቅስቃሴ ላይ እንቅፋትና ስጋት ይፈጥርብናል፡፡ በየክልሉ ተንቀሳቅሰን የፓርቲውን ስራ መስራት አለብን፣ ከህዝብ ዘንድ መድረስ አለብን፡፡ ይሄን ለማድረግ እንዴት ፍቃድ እናገኛለን፡፡ ይሄ በጣም ይከብዳል። በጣም ያሳስበናል፡፡ ፓርቲያችን በዚህ ጉዳይ ተሰብስቦና መክሮበት አቋሙን በመግለጫ የሚያሳውቅ ይሆናል፡፡

=================================

“የአዋጁ መራዘም ለኔ አስደንጋጭና አሳዛኝ ነው”

ፕ/ር በየነ ጴጥሮስ (የመድረክ ሊቀመንበር)

የአዋጁ መራዘም ለኔ አስደንጋጭ ነው፡፡ የስጋታችንን ደረጃ የበለጠ እያጠለቀው ነው፡፡ እነሱ ተሃድሶአችንን እያጠለቅን ነው እንደሚሉት ሁሉ የኛም ስጋት እንዲሁ ደረጃው እየጠለቀ ነው ያለው፡፡ ይሄ አዋጅ መፍትሄ አይሆንም፡፡ እነሱ ህዝብን አስገድዶ እየገዙ መኖር የሚለውን የቻይናዎች ፍልስፍና ነው እየተከተሉ ያሉት፡፡ የተለያዩ ፍላጎቶችና ጥያቄዎች ያላቸው ህዝቦችን በምታስተናግድ ሀገር ላይ የዚህ ዓይነት አካሄድ በብሶት ላይ ብሶት፣ በምሬት ላይ ምሬት ይፈጥራል። ህዝቡን ለማስከፋት ምክንያት መጨመር ነው የሚሆነው፡፡ ይሄ በዚህ ሀገር በጣም አሳዛኙ አጋጣሚ ነው፡፡ የዚህ አይነቱ እርምጃ ለኛ አይነቱ ሀገር የሚሆን አይደለም፡፡ እነዚህ ሰዎች ምን ያህል ራዕይ እንዳጡና ምን ያህል ፍርሃት ውስጥ እንዳሉ ነው የሚያሳየው፡፡
4 ወር እኮ አሁንም ያልቃል፡፡ ከዛ ምን ይፈጠራል? 6 ወር ምንም ሳይሰራ አይደለም እንዴ ያለቀው፡፡ መፍትሄው ይሄ አይደለም፤ ዝም ብሎ ድብብቆሽ እንደሚጫወቱ ህፃናት መሆን ነው፡፡ እኔ ብዙም የፖለቲካ ጥበብ አላየሁበትም። ህዝቡ በነፃ ሃሳቡን ገልፆ መንቀሳቀስ ሲችል እኮ ነው መንግስት የህዝብን ሀሳብ መረዳት የሚችለው፡፡ በሀዘንና በምሬት አንገቱን ደፍቶ ውስጡ እየፋመ መኖሩ አስቸጋሪ ሁኔታ ይፈጥራል፡፡ ታምቆ የከረመ ነገር ፈንድቶ ሲወጣ ጉዳቱ ኃይለኛ ነው የሚሆነው። ስለዚህ በብሶት ላይ ብሶት እየጨመሩ መሄድ የበለጠ ነገር ከማወሳሰብ ውጪ በሀገሪቱ ለተነሱት ጥያቄዎች ምላሽ ይሆናል የሚል እምነት የለኝም። የተወሰደውም እርምጃ አግባብ አይደለም፡፡ ህዝባችንም ትዕግስቱን አሳይቷል፡፡ ህገ መንግስቱ የሰጣቸው 4 ወር ጊዜ ካለቀ በኋላ ደግሞ ምን እንደሚፈበርኩ ለማየት የዚያ ሰው ያድርገን ነው የምንለው፡፡
በዚህ መሀል  የአባላቶቻችን መታሰር፣ የሰብአዊ መብት መጣስ ስጋታችን ያይላል ማለት ነው። ምን ተፈጥሮ ነው የሚያራዝሙት? ምን ስጋት ታያቸው? ከተፈለገም ችግር ባለባቸው ቦታዎች ብቻ ማራዘም ይቻል ነበር፡፡ አሁን አዲስ አበባ ምን ችግር ታየ? በሌሎች አካባቢዎችስ? ጠቅላይ ሚኒስትሩ፤”80 ከመቶ በላይ ህዝብ እንዲራዘም ፈልጓል” ብለው ሲናገሩ፣ እንደ ሀገር መሪ ጥንቃቄ ማድረግ የለባቸውም እንዴ? የትኛው ድርጅት ነው ይሄን ያጠናው? ምናልባት ኢህአዴግ ካድሬዎቹን አነጋግሮ ሊሆን ይችላል፡፡ ብቻ ማን ጠያቂ አለብኝ እየተባለ ነው ሁሉም ነገር የሚደረገው፡፡ እንግዲህ ሁላችንም ተስፋ ቆርጠን … ቆርጠን የዚህች ሀገር ነገር ምን እንደሚሆን ያስጨንቃል፡፡  

===================================


“አሁንም ቢሆን
የሚያስፈልገው የፖለቲካ መፍትሄ ነው”

ዶ/ር ጫኔ ከበደ (የኢዴፓ ፕሬዚዳንት)

አዋጁን ማራዘም ባለፉት 6 ወራት ታይቶ የነበረውን የኢኮኖሚ ውድቀት በድፍረት ማስቀጠል ነው፡፡ አጠቃላይ የማህበራዊ ኢኮኖሚ ሂደቱ ሙሉ ለሙሉ ወድቋል፡፡ ከእድገት አንፃር፣ ከGTP 2 አንፃር፣ ከጤናና ከትምህርት አንፃር-----በሌሎችም ዘርፎች ታስቦ የነበረው የእድገት እቅድ ሙሉ ለሙሉ ወደ ተግባር የማይቀየርበት ጊዜ ይመጣል ብለን እናስባለን፡፡ አዋጁ ተራዘመ ማለት የኢኮኖሚ እንቅስቃሴዎች በሙሉ በነበሩበት ደካማ አካሄድ ይቀጥላሉ ማለት ነው፡፡ ሌሎች  መንግስትም ባለሀብቶችም የሚያካሂዷቸው ኢንቨስትመንቶች በሙሉ እየተጎዱ ነው የሚሄዱት፡፡
አሁንም ፖለቲካዊ መፍትሄ እስካልመጣ ድረስ 4 ወር ቢራዘም ምንም አይነት ለውጥ የሚያመጣ መስሎ አይታየኝም፡፡ ህዝቡ እስካሁን የጠየቃቸው ጥያቄዎች እየተመለሱለት አይደለም ብዬ ነው የማስበው፡፡
በዚህ ጊዜ ውስጥ ጥልቅ ተሃድሶ ተብሎ እስከ ታች የወረደውን አካሄድ ለማየት ሞክረን ነበር፡፡ ነገር ግን ሰዎች ከቦታ ቦታ ተዘዋወሩ እንጂ የማያሰሩ ደንቦችና ህጎች ሪፎርም አልተደረጉም፡፡ ክፍተቶቹ እንዳሉ ናቸው፤አሁንም አልተዘጉም፡፡ ስለዚህ አዋጁ ለውጥ አምጥቷል ማለት አይቻልም፡፡ ለ4 ወር ብቻ ሳይሆን ለቀጣይ አንድ ዓመት ራሱ በዚህ መንገድ ከቀጠለ ህዝቡ የበለጠ ወደ ሌላ አማራጭ እንዲያመራ በር እየከፈተ ነው የሚሄደው፡፡
 አሁን እንደምናየው በየመንደሩ ሚሊሻና ካድሬ የተለየ አስተሳሰብ ያለውን የህብረተሰብ ክፍል እያሰረ ነው ያለው፡፡ ባለፉት ጊዜያት አንድም አባል ታስሮብን የማናውቅ ፓርቲ፣ አሁን በየወረዳዎቹ አባሎቻችን ታስረውብን ነው ያሉት፡፡ ይሄ የበለጠ ጥላቻን፣ ቅራኔንና ቂምን እየቋጠረ ነው የሚሄደው፡፡ ህብረተሰቡ አሁን ባለው አኳሃን የተሻለ አስተሳሰብ ይይዛል ብለን አናስብም፡፡ አሁንም ቢሆን የሚያስፈልገው የፖለቲካ መፍትሄ ነው፡፡ ውይይት ነው የሚያስፈልገው፡፡ ውይይቱን ራሱ እናድርግ ስንል እንኳ ምን ያህል እየገፋን እንደሆነ እየታየ ነው። የአስቸኳይ ጊዜ አዋጁ መነሳት እንዳለበት፣ የታሰሩ ሰዎች መፈታት እንዳለባቸው በአጀንዳ መልክ እንወያይበታለን ያልነው ሁሉ ዘግተውብናል፡፡
ላለፉት 20 ዓመታት ያለፉበትን የፖለቲካ ሂደት መገምገም አይከብደንም፡፡ በአጠቃላይ ስጋት እየጫሩ ነው ያሉት፡፡ እነሱም ይሰጋሉ፡፡ እንዳያሻሽሉ ግራ ገብቷቸዋል፡፡ እንዳያሳትፉን ደግሞ በመሃል ብዙ ሚስጥሮች ይወጣሉ፡፡ እነዚህ ነገሮች በሙሉ ለነሡ ስጋት ሆነው ነው የሚቀጥሉት፡፡
እንደሚታወቀው በሃገሪቱ ላይ የውጭ ምንዛሬ ጠፍቷል፡፡ ምንዛሬ ጠፋ ማለት ወጪ ገቢ ንግድ መስራት አይቻልም ማለት ነው፡፡ ትላልቅ ባለሃብቶች በምንዛሬ እጥረት ምክንያት ሠራተኛ እየቀነሱ ነው ያሉት፡፡ ምርት እየቀነሱ ነው፡፡ የኢንዱስትሪ ዞን ተብለው የተቋቋሙ ማዕከላት በገንዘብ እጥረትና በአዋጁ ምክንያት በሙሉ አቅማቸው እየሠሩ አይደለም፡፡ በዚህ የተነሳ  አገሪቱ በኢኮኖሚ ምን ያህል እየተጎዳች እንደሆነ መገመት አያዳግትም፡፡ ይሄን ሁሉ ባለማሰባቸው አዋጁ መራዘሙ እስካሁን ከነበረው እጅግ የበለጠ እየጎዳን ነው የሚሄደው፡፡ ሰላምና መረጋጋትን ማምጣት የሚቻለው አዋጁን በማስቀጠልና በመዋሸት አይደለም፡፡ አንድ ታላቅ የሃገር መሪ የሆነ ሰው፤”82 በመቶ ህዝብ እንዲቀጥል ደግፎናል” ብሎ የሚናገርበት የውሸት አለም ላይ ነው ያለነው፡፡ መቼ ሄደው መረጃ ሰብስበው ነው? መቼ ህዝብ የሚናገረውን አደመጡ?... እንዲህ ያለ ሃሰተኛ መረጃ በአደባባይ መናገር እጅግ ያሳዝናል። መቼም አሁን ባለንበት ደረጃ አንቀርም፡፡ ተተኪው ትውልድም ቢሆን የለውጥ ጥያቄ አንግቦ ጥያቄ የሚያቀርብበት ጊዜ ሩቅ ይሆናል ብለን አናስብም፡፡
============================


‹‹አዋጁ መራዘሙ ለችግሩ መፍትሄ አይሆንም››
ዶ/ር በዛብህ ደምሴ (የመኢአድ ፕሬዚዳንት


በሌላው አለም የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ ችግር ያለበት ቦታ ላይ ብቻ ተለይቶ ነው የሚታወጀው፡፡  እንደኛ ሃገር እንደዚህ የተራዘመ አዋጅ አይጣልም፡፡ መንግስት የአስቸኳይ ጊዜ አዋጁን ከማራዘም ይልቅ “ለምንድን ነው ህዝቡ በየክልሉ ብሶቱን የገለፀብኝ ?”፣ “ምንድን ነው የጠየቀው?” የሚለውን አጢኖ፣መልስ ለመስጠት ቢሞክር ነበር የሚያዋጣው፡፡ የአስቸኳይ ጊዜ አዋጁ መራዘሙ ተገቢ ነው ብዬ አልገምትም፡፡ መንግስት እንደ መንግስትነቱ ለህዝቡ ብሶት መልስ መስጠት እንጂ በጉልበትና በሃይል ዘላቂ መፍትሄ አያመጣም፡፡
ይሄ መንግስት ሁሉም እንደሚያውቀው ሠላም፣ እድገት እያለ ይናገራል፡፡ ሁሉም የኢትዮጵያ ህዝብ ደግሞ ሠላምም እድገትም ይፈልጋል፤ግን ሠላምና እድገት ሊመጣ የሚችለው ዝም ብሎ በምኞት ሳይሆን ህዝቡ ለሚጠይቀው ጥያቄ መንግስት ተገቢውን መልስ መስጠት ሲችል ብቻ ነው፡፡ በኔ እምነት አዋጁ መራዘሙ ለችግሩ መፍትሄ ይሆናል ብዬ አልገምትም፡፡
በአሁኑ ጊዜ የፓርቲያችን አባላትና አመራሮች ይታሰራሉ ይፈታሉ፡፡ እርግጥ ነው ለኮማንድ ፖስቱ አመልክተን የተፈቱልን አባላት አሉ፡፡ ግን በአጠቃላይ የፖለቲካ እንቅስቃሴያችንን ገድቦታል። አባሎቻችን እንደ ልባቸው ተሰብስበው ውይይት ለማድረግ ተቸግረዋል፡፡

ጽላቱን የሚያውቁ ካህናት በምርመራው መካተት እንዳለባቸው ተጠቁሟል
• “ጥያቄውን ለሀገረ ስብከቱ እንዳናቀርብ ሥራ አስኪያጁ ያሳስሩናል” /ምእመናኑ

በጋምቤላና ደቡብ ሱዳን አህጉረ ስብከት መንበረ ጵጵስና የምትገኘው፣ የሐመረ ኖኅ ቅድስት ኪዳነ ምሕረት ካቴድራል ዕድሜ ጠገብ ታቦት፣ የደረሰበት አለመታወቁን የከተማው ምእመናን የተናገሩ ሲሆን፤ በአቋራጭ መክበር በሚፈልጉ ስግብግቦች እጅ ሳይገባ አፋጣኝ ማጣራትና ምርመራ እንዲካሔድላቸው መንበረ ፓትርያርኩን ጠየቁ፡፡
ቤተ ክርስቲያኒቱ፣ በንጉሠ ነገሥት ዐፄ ኃይለ ሥላሴ ትእዛዝ በ1941 ዓ.ም. መታነጿንና ሙሉ በሙሉ በወርቅ የተለበጠ የኪዳነ ምሕረት ታቦትም እንዲገባ ካስደረጉ በኋላ፣ ሥርዓተ እምነታቸውን ሲፈጽሙባትና ሲማፀኑባት እንደኖሩ ምእመናኑ ጠቅሰው፤ ከየካቲት 24 ቀን ጀምሮ ግን ታቦቱ በመንበሩ ላይ እንደሌለ ከካቴድራሉ ካህናት መስማታቸውን ተናግረዋል፡፡
የታቦቱ/ጽላቱ/ በመንበሩ ላይ አለመኖር በመጀመሪያ ያረጋገጡት የካቴድራሉ አስተዳዳሪ እንደነበሩና ጉዳዩ በቀጥታ የሚመለከታቸውን ቄሰ ገበዙን እንደጠየቋቸው ያወሱት ምእመናኑ፣ ቄሰ ገበዙ፥ “እኔን ለምን ትጠይቁኛላችሁ? ሥራ አስኪያጁን ጠይቁ፤” የሚል ምላሽ በመስጠታቸው፣ “ሁኔታውን ይበልጥ አሳሳቢ አድርጎብናል፤” ብለዋል፡፡ በቀጥታ ለጋምቤላ ሀገረ ስብከት ሥራ አስኪያጅ እንዳያቀርቡ፣ “የአስቸኳይ ጊዜ ዐዋጁን ተጠቅመው ያሳስሩናል፤” ብለው እንደሚሰጉና ሁከት እንዳይቀሰቀስ ፍርሃት እንዳደረባቸው ምእመናኑ አልሸሸጉም፡፡
“ለምነን ያላፈርንባት፤ ችግራችንን ፈጥና የምትሰማን የኪዳነ ምሕረት ታቦት ጠፍታ እንዴት ዝም እንላለን፤ ብለን በአንድ ቦታ ተሰብስበን ከተመካከርን በኋላ በትዕግሥትና በሥርዓት ለሚመለከተው የበላይ አካል ማመልከትን መርጠናል፤” ያሉት ምእመናኑ፣ ወደ አዲስ አበባ በመምጣት፣ ባለፈው መጋቢት 13 እና 14 ቀን፣ ጉዳዩን ለቅዱስ ሲኖዶስ ጽ/ቤት፣ ለመንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ቤተ ክህነት ጽ/ቤትና ለፓትርያርኩ ልዩ ጽ/ቤት ማቅረባቸውን አስታውቀዋል፡፡
ሙሉ በሙሉ ከወርቅ የተሠራው ታቦት፣ የሀገርም ቅርስ መሆኑን ምእመናኑ ጠቁመው፣ በአቋራጭ የመክበር ምኞት በተጠናወታቸው ስግብግቦች እጅ ሳይገባ፣ በመንበረ ፓትርያርኩ መሪነት አስቸኳይ ማጣራትና ምርምራ እንዲካሔድላቸው ተማፅነዋል፤ ጽላቱ የሚቀመጥበት መንበር ባዶ መኾኑን የሚያሳይ በወቅቱ የተቀረፀ የቪዲዮ ምስል በአባሪነት ማቅረባቸውን ገልጸው፣ ጽላቱ በመንበሩ ላይ ተገኘ ቢባል እንኳ፣ ዕድሜ ጠገቡ ጽላት መሆኑን ለይተው በሚያውቁ ካህናት ታይቶ መረጋገጥ እንደሚኖርበት ጨምረው አሳስበዋል፡፡
አህጉረ ስብከቱን በዋና ሥራ አስኪያጅነት የሚመሩት መጋቤ አእላፍ ቆሞስ አባ ተክለ ሃይማኖት፣ በክልሉ ተመድበው በሠሩበት ባለፉት ዘጠኝ ዓመታት፣ 17 ብቻ የነበሩት አብያተ ክርስቲያናት ቁጥር ወደ 53 ማደጉንና በደቡብ ሱዳን ጭምር መታነፃቸው ተገልጧል፡፡ ይህም የዋና ሥራ አስኪያጁን ሐዋርያዊ ትጋት ያመለክታል ቢባልም፣ በአገልግሎታቸው ቀጣይነትና አያያዝ ረገድ፣ ከአገልጋዮችና ምእመናን በርካታ ጥያቄዎች እየተነሡ እንደሚገኙ ተጠቁሟል፡፡
ወደ ማተሚያ ቤት እስከገባንበት ሰዓት ድረስ፣ የሀገረ ስብከቱን ዋና ሥራ አስኪያጅ በእጅ ስልካቸው ላይ በመደወል አስተያየታቸውን ለማካተት ያደረግነው ተደጋጋሚ ጥረት አልተሳካም፡፡



የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያንን አስተምህሮ ይፃረራል፤ ያሉት የትግርኛ ቋንቋ ትርጉም መጽሐፍ ቅዱስ ከሥርጭት እንዲታገድላቸውና እንዲወገድላቸው፣ የመቐለ ምእመናን የጠየቁ ሲሆን፤ የኢትዮጵያ መጽሐፍ ቅዱስ ማኅበር በበኩሉ፣ “ትርጉሙ፣ በቤተ
ክርስቲያኗ ሊቃውንት የተሠራ ነው፤ ስሕተት አለው፤ የሚል እምነት የለንም፤” ብሏል፡፡
ከ40 በላይ የሆኑ ምእመናን የተፈራረሙበት ማመልከቻ፤ ለትግራይ አህጉረ ስብከት 4 ሊቃነ ጳጳሳት በግንቦት 2008 ዓ.ም ያቀረቡ ቢሆንም፤ ለጥያቄያቸው እስከ አሁን ምላሽ እንዳልተሰጣቸው ምዕመናኑ ለአዲስ አድማስ አስታውቀዋል፡፡
የኦርቶዶክስ፣ የካቶሊክ እና የወንጌላውያን ኅብረት አብያተ ክርስቲያናት አባል የሆኑበት የኢትዮጵያ መጽሐፍ ቅዱስ ማኅበር ያሳተመው ይህ መጽሐፍ ቅዱስ፤ “ከኦርቶዶክስ ተዋሕዶ አስተምህሮ በተፃራሪ፡- የክርስቶስን የባሕርይ አምላክነት የሚክድ፣ የቅድስት ሥላሴን አንድነትና ሦስትነት የሚያዛባ፣ ሥልጣነ ክህነትን የሚሽርና የማይቀበል፣ የቤተ ክርስቲያኗን ፊደልና ቁጥር አቆጣጠር የማይቀበል እንዲሁም፣ ቤተ ክርስቲያኗ የምትቀበላቸውን 81 መጽሐፍ ቅዱስ ወደ ጎን በመተው 66 መጻሕፍትን ብቻ ያካተተ በመሆኑ፣ እምነትን የሚያስክድ ነው፤ ይወገድልን፤” ብለዋል - ምዕመናኑ፡፡
መጽሐፍ ቅዱሱ ታትሞ በገበያ ላይ ከዋለ በኋላ፣ 92 በመቶ የሚሆነውን የክልሉን የኦርቶዶክስ ተዋሕዶ እምነት ተከታይ ግራ እያጋባ መሆኑንም ምዕመናኑ በማመልከቻቸው ጠቁመዋል፡፡ የቤተ ክርስቲያኒቱን ዶግማ ይፃረራል፤ የተባለው ይኸው መጽሐፍ ቅዱስ፣ ወደተለያዩ የከተማና እና የገጠር አብያተ ክርስቲያናት እንዳይሰራጭና

ዳግመኛም እንዳይታተም እንዲታዘዝላቸው ምዕመናኑ ጠይቀዋል። የትርጉሙን ስሕተት የሠሩ አካላትም ተጠያቂ እንዲሆኑና ርምጃ

እንዲወሰድባቸው ምዕመናኑ አያይዘው ጠይቀዋል።
በጉዳዩ ላይ ያነጋገርናቸው የኢትዮጵያ መጽሐፍ ቅዱስ ማኅበር ጠቅላይ ጸሐፊ፣ መምህር ይልማ ጌታሁን፣ ለመጽሐፍ ቅዱስ ማኅበር በግልጽ የቀረበ

አቤቱታ እንደሌለ ገልጸው፣ አቤቱታ አቅራቢዎች ለቤተ ክርስቲያኒቱ ቅሬታ አቅርበው፣ ቤተ ክርስቲያኒቱ ጉዳዩን እያየችው መሆኑን መረጃ

እንዳላቸው ጠቁመዋል፡፡
ትርጉሙ፣ በኢ/ኦ/ተ/ቤ/ክርስቲያን ሊቃውንት በጥንቃቄ የተሠራ መሆኑን የጠቆሙት መምህር ይልማ፣ “ሥራው ስሕተት አለው ብለን አናምንም፤

አለው ቢባል እንኳ ሊቃውንቱን ነው መጠየቅ ይችሉ የነበረው፤” ብለዋል፡፡ የትርጉም ሥራው፣ በሊቃውንት ተመርምሮ ፓትርያርኩ ባሉበት

ተመርቆ እንዲሰራጭ መደረጉንም መምህር ይልማ አስረድተዋል፡፡
“ትርጉሞች፣ በቤተ ክርስቲያን ፈቃድና ተሳትፎ የሚሠሩ ናቸው እንጂ፣ ማኅበሩ በራሱ ተነሣስቶ የሚያደርገው አይደለም፤” ያሉት መምህር ይልማ፤

እስከ አሁንም፣ የትርጉም ስሕተት አለበት፤ የሚል ጥቆማ ለማኅበሩ እንዳልቀረበ አስታውቀዋል፡፡ 

   በሚያዚያ ወር በጥቅል ‹‹ሶስታ ሃሴት›› የሚል ሰያሜ የተሰጣቸው 3 ተከታታይ ሩጫዎች ተዘጋጅተዋል

       በተባበሩት መንግስታት አብይ ስፖንሰርነት ‹‹ስለምትችል››  በሚል መርህ ከሳምንት በፊት ለ14ኛ ጊዜ የተካሄደው  የታላቁ ሩጫ በኢትዮጵያ ቅድሚያ ለሴቶች የ5 ኪ.ሜ የጎዳና ላይ ሩጫ ስኬታማ እንደነበር የውድድሩ አስተባባሪ  ዳግማዊት አማረ ለስፖርት አድማስ ገለፀች፡፡
11ሺ ተሳታፊዎች የነበሩት የጎዳና ላይ ሩጫው መነሻ እና መድረሻው በመደበኛው  አትላስ ሆቴል  መመለሱ ድምቀት ፈጥሯል ያለችው ዳግማዊት፤  ሩጫው ከመጀመሩ በፊት እና ካበቃ በኋላ የነበረው አጠቃላይ ድባብ ያማረ ነበር ብላለች፡፡ ውድድሩ ከመጀመሩ በፊት ከ150 ዓመታት በፊት ስለነበረች የኢትዮጵያ ጀግና ሴት የተሰራው የቃቄ ውርድዎት  ቲያትር አንድ የተቀነጨበ ትዕይነት ለእይታ መቅረቡ፤ በሴቶች እየተዘወተረ የመጣው ታዋቂው የዙምባ ዳንስ ደስ የሚል ትርኢቶችን በመፍጠር ውድድሩን ማሟሟቁ፤ እንዲሁም ስለምትችል የሚለው መርህን በማንገብ የሴቶችን ስኬትና ሚና ለማክበር የተደረጉት እንቅስቃሴዎች ስኬታማ እንደነበሩም አብራርታለች፡፡
በ5 ኪ.ሜትር የጎዳና ላይ ሩጫው በዋናው የአዋቂ አትሌቶች ውድድር አስደናቂ ውጤት የተመዘገበ ሲሆን በመሰረት ደፋር በባለቤቷ ቴድሮስ የሚንቀሳቀሰው የአዲዳስ  ዴፕሎፕመንት ፕሮጀክት ወጣት አትሌቶች ብዙም የውድድር ልምድ ባይኖራቸውም በአንደኛ እና  ሁለተኛ ደረጃ ውድድሩን በመጨረሳቸው ነበር፡፡ በ1ኛ ደረጃ የጨረሰችው የአዲዳስ ዴቨሎፕመንት አትሌት ደጊቱ አዝመራው ስትሆን ሌላዋ አጋሯ አበባ ተፈራ በሁለተኛ ደረጃ ተከትላ ገብታለች፡፡ ምህረት ተፈራ እና ብርሃን ምህረቱ ከሱር ኮንስትራክሽን 3ኛእና አራተኛደረጃ አግኝተዋል፡፡  በሌላ በኩል ከ35 ደቂቃ በታች 5 ኪሎሜትሩን ለሚጨርሱ  ስፖርተኞች ከሜዳልያ ሽልማት ባሻገር የአትሌት መሰረት ደፋር ፊርማ ያረፈበት 2000 ሰርተፍኬቶች ለሽልማት የቀረቡ ቢሆንም፤ በውድድሩ ላይ  ከ35 ደቂቃ በታች በመጨረስ የተሸለሙት 300 ብቻ ሆነዋል፡፡ በውድድሩ መነሻ ላይ በአንድ ጎዳና ላይ እጅብ ብሎ በመሮጥ የተፈጠረው  ግርግርና መጨናነቅ ብዙ ሴቶች ከ35 ደቂቃ በታች ውድድራቸውን እንዳይጨርሱ አድርጓቸዋል ብላለች፡፡ ዳግማዊት አማረ ከታላቁ ሩጫ በኢትዮጵያ  ፡፡ ከ30 በላይ ስፖርተኞችን ባሳተፈው የሴት ተምሳሌቶች  ውድድር የግሸን ፋርማሲ ባለቤት ወይዘሮ አማከለች ሉሉ ሲያሸነፉ በሁለተኛደረጃ የጨረሰችው ድምፃዊት ቤተልሄም ጌታሁን ወይም ቤቲ ጂ ነበረች፡፡ በአምባሳደርና የውጭ ዲፕሎማቶች ምድብ ደግሞ የስውድን አምባሳደር ባለቤት ሚስሪኮ ሜንሲያ  አሸንፈዋል፡፡    
ይህ በእንዲህ እንዳለ ታላቁ ሩጫ በኢትዮጵያ ከሚያዚያ 15  ጀምሮ  ባሉት ተከታታይ 3 እሁዶች የተለያዩ 3 ሩጫዎችን ማዘጋጀቱን ለስፖርት አድማ በላከው መግለጫ ያመለከተ ሲሆን ሶስቱ ተከታታይ ሩጫዎች በጥቅል ሶስታ ሃሴት (Triple Crown) የሚል ስያሜ ሰጥቷቸዋል፡፡ የመጀመርያው ሚያዚያ 15 የሚካሄደውና በአጠቃላይ 4000 ተሳታፊዎችን የሚያስተናግደው የሃዋሳው 2009 ሲሲኢሲሲ ሃዋሳ ግማሽ ማራቶን ሲሆን ይህ ሩጫ በውስጡ የ21 ኪ.ሜ.፤ የ7ኪ.ሜ እንዱሁም የህፃናት ሩጫ የሚያካትት ይሆናል፡፡  ሁለተኛው ውድድር
ታላቁ ሩጫ በኢትዮጵያ ከኢትዮጵያ ህክምና ባለሞያዎች ማህበር ጋር በመሆን የሚያዘጋጀው አመታዊው ኤማ ሩጫ  ሚያዚያ 22 ቀን ለ2ኛ ጊዜ ሲካሄድ  5000 ተሳታፊዎች ይኖሩታል፡፡
በመጨረሻም ሚያዚያ 29 ላይ የአውሮፓ ቀንን አስመልክቶ የሚዘጋጀው የአውሮፓ ቀን የህፃናት ሩጫ ሲሆን እድሜያቸው ከ3 አመት በላይ የሆኑ 3000 ህፃናት ወንዶችና ሴቶችን  የሚሳተፉበት ይሆናል፡፡

    በ12 ወራት 1 ቢ. ዶላር የከሰሩት ትራምፕ፣ ከአምናው ደረጃቸው በ220 ዝቅ

       ላለፉት ሶስት አመታት የአለማችን ቁጥር አንድ ቢሊየነር ሆነው የዘለቁት አሜሪካዊው የማይክሮሶፍት መስራች ቢል ጌትስ፣ ዘንድሮም የአለማችን ቁጥር አንድ ባለጸጋ መሆናቸውን ታዋቂው ፎርብስ መጽሄት በሳምንቱ መጀመሪያ ላይ ይፋ ባደረገው የ2016 የፈረንጆች አመት የአለማችን ቢሊየነሮች ዝርዝር አስታውቋል፡፡
አምና በ75 ቢሊዮን ዶላር የተጣራ ሃብት የአለማችን ቀዳሚው ቢሊየነር የነበሩት ቢል ጌትስ፣ በአንድ አመት ውስጥ የሃብት መጠናቸው በ11 ቢሊዮን ዶላር በማደግ 86 ቢሊዮን ዶላር መድረሱንና ዘንድሮም በመሪነታቸው መቀጠላቸውን ያስታወቀው ፎርብስ፤ ቢል ጌትስ ካለፉት 23 አመታት በ18ቱ የአለማችን ቁጥር አንድ ቢሊየነር መሆን መቻላቸውንም አስታውሷል፡፡
አሜሪካዊው ዋረን ቡፌት በ75.6 ቢሊዮን ዶላር ሁለተኛው የአለማችን ባለጸጋ ሆነዋል ያለው መጽሄቱ፤ በአመቱ ከአለማችን ቢሊየነሮች ከፍተኛው የተባለለትን የ27.6 ቢሊዮን ዶላር የሃብት ጭማሪ በማስመዝገብ አጠቃላይ ሃብታቸው 72.8 ቢሊዮን ዶላር የደረሰላቸው የአማዞን ኩባንያ መስራች ጄፍ ቤዞስ ሶስተኛ ደረጃን መያዛቸውን አስረድቷል፡፡
የአሜሪካው ፕሬዚዳንት ዶናልድ ትራምፕ በፖለቲካው የተጎናጸፉትን ድል በቢዝነሱ ለመድገም አልቻሉም ያለው ፎርብስ፤ ትራምፕ በአመቱ የሃብት መጠናቸው በ1 ቢሊዮን ዶላር ቅናሽ አሳይቶ 3.5 ቢሊዮን ዶላር በመድረሱ፣ አምና ከነበሩበት ደረጃ በ220 በማሽቆልቆል 554ኛ ደረጃ ላይ መቀመጣቸውን ገልጧል፡፡
በዘንድሮው የፎርብስ የቢሊየነሮች ዝርዝር ውስጥ በድምሩ 1 ትሪሊዮን ዶላር የተጣራ ሃብት ያላቸው 183 የቴክኖሎጂው ዘርፍ ባለጸጎች የተካተቱ ሲሆን፣ በ12 ወራት ጊዜ ውስጥ 11.4 ቢሊዮን ዶላር በማፍራት የሃብቱን መጠን 56 ቢሊዮን ዶላር ያደረሰው የፌስቡኩ መስራች ማርክ ዙክበርግ በአምስተኛ ደረጃ ላይ ተቀምጧል፡፡
የአለማችን ቢሊየነሮች ብዛት አምና ከነበረበት የ13 በመቶ እድገት በማሳየት፣ 2 ሺህ 43 መድረሱን ያስታወቀው ፎርብስ፤አሜሪካ 565 ቢሊየነሮችን በዝርዝሩ ውስጥ በማካተት ቀዳሚነቱን መያዟን፣ ቻይና በበኩሏ 319 ቢሊየነሮችን በማስመዝገብ ሁለተኛ ደረጃ ላይ መቀመጧን ገልጧል፡፡
የሴት ቢሊየነሮች ቁጥር አምና ከነበረበት 202 ወደ 227 ማደጉ የተነገረ ሲሆን 39.5 ቢሊዮን ዶላር የተጣራ ሃብት ያላት ፈረንሳዊቷ ሌላኔ ቤቴንኮርት እንደ አምናው ሁሉ ዘንድሮም የአለማችን ቁጥር አንድ ሴት ቢሊየነር ሆናለች፡፡
በአመቱ ወደ ፎርብስ የቢሊየነሮች ዝርዝር የገቡ አዳዲስ ባለጸጎች ቁጥር 195 ሲሆን፣ አብዛኞቹ ቻይናውያን መሆናቸው ተነግሯል፡፡ በአንጻሩ ደግሞ፣ የሃብት መጠናቸው በማሽቆልቆሉና ከዚህ አለም በሞት በመለየታቸው ሳቢያ ከዝርዝሩ ውስጥ የተወገዱ ባለጸጎች ቁጥር 78 ነው ተብሏል፡፡
በዘንድሮው  የአለማችን ቢሊየነሮች ዝርዝር ውስጥ የተካተቱት 2 ሺህ 43 ቢሊየነሮች አጠቃላይ ድምር የተጣራ ሃብት 7.67 ትሪሊዮን ዶላር እንደሚደርስም ፎርብስ መጽሄት ሰኞ ዕለት ባወጣው መረጃ አስታውቋል፡፡

የሰሜን ኮርያ የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ቃል አቀባይ፣ አሜሪካ በሰሜን ኮርያ ላይ ወታደራዊ እርምጃ ልወስድ እችላለሁ  በሚል በይፋ ማስጠንቀቋ፣ አገራቸውን ፍርሃት ውስጥ እንደማይከታትና የኒውክሌርና የሚሳየል ፕሮግራሞቿን ከማካሄድ እንደማይገታት ማስታወቃቸውን አሶሼትድ ፕሬስ ዘግቧል፡፡
የአሜሪካ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ሬክስ ቲለርሰን ባለፈው አርብ በሰጡት መግለጫ፣ አገራቸው በሰሜን ኮርያ ላይ ጠበቅ ያለ ማዕቀብ እንደምትጥልና ወታደራዊ እርምጃ ልትወስድ እንደምትችል ማስጠንቀቃቸውን ያስታወሰው ዘገባው፤ የሰሜን ኮርያው ቃል አቀባይ በበኩላቸው ለአገራቸው የዜና ወኪል በኩል በሰጡት ምላሽ፣ አገራቸው በአሜሪካ ዛቻ እንደማትደናገጥ መግለጻቸውን አስታውቋል፡፡
የሰሜን ኮርያ ኒውክሌር አገሪቱንና ህዝቦቿን ከጥፋት የሚታደግ ሁነኛ መሳሪያ ነው ያሉት ቃል አቀባዩ፤ ሰሜን ኮርያ ከአሜሪካ ሊቃጣባት የሚችልን ወታደራዊ ጥቃት በብቃት ለመመከት በሚያስችል ሁኔታ ኒውክሌር የታጠቀች አገር መሆኗን መሪዎቿ ሊገነዘቡ ይገባል ማለታቸውንም ዘገባው ገልጧል፡፡
ከንግድ ወደ ፖለቲካ ፊታቸውን ያዞሩት የአሜሪካ ባለስልጣናት፣ ሰሜን ኮርያን በዛቻና በማስፈራሪያ ትሸማቀቃለች ብለው የሚያስቡ ከሆነ ተሳስተዋል፤ መሳሳታቸውንም በቅርቡ ይገነዘባሉ ሲሉም አክለዋል፡፡
ምንም አይነት የኒውክሌርም ሆነ የሚሳኤል ሙከራ እንዳታደርግ ከተባበሩት መንግስታት ድርጅት ክልከላ የተደረገባትና በኒውክሌር ፕሮግራሟ ሳቢያ ከአሜሪካ ጋር ግጭት ውስጥ የገባቺው ሰሜን ኮርያ፤ ባለፈው የፈረንጆች አመት ብቻ ለሁለት ጊዚያት የኒውክሌር ሙከራ ፍንዳታዎችን፣ ለ24 ጊዚያት ያህል ደግሞ የባለስቲክ ሚሳኤል ሙከራዎችን ማድረጓን ዘገባው አስታውሷል፡፡

 ከሰሞኑ ይፋ የተደረገው የ2017 የአለማችን አገራት የደስተኛነት ደረጃ ሪፖርት፣ ኖርዌይን ከ155 የአለማችን አገራት በቀዳሚነት ሲያስቀምጥ፣ የመካከለኛው አፍሪካ ሪፐብሊክ ደግሞ በመጨረሻ ደረጃ ላይ ትገኛለች ማለቱን ኒውዮርክ ታይምስ ዘግቧል፡፡ ስድስት ያህል የአገራትን ማህበረ-ኢኮኖሚያዊ ሁኔታ መመዘኛ መስፈርቶችን በመጠቀም በየአመቱ የአገራትን የደስተኛነት ደረጃ ይፋ የሚያደርገው ሰስቴኔብል ዲቨሎፕመንት ሶሊዩሽንስ ኔትወርክ የተባለው አለማቀፍ ተቋም፣ በ2017 ሪፖርቱ ዴንማርክን በሁለተኛ፣ አይስላንድን በሶስተኛ ደረጃ ላይ አስቀምጧቸዋል፡፡
ስዊዘርላንድ፣ ፊላንድ፣ ኒዘርላንድስ፣ ካናዳ፣ ኒውዚላንድ፣ አውስትራሊያ እና ስዊድን ተከታዮቹን ደረጃዎች መያዛቸው የተነገረ ሲሆን፣ ዴንማርክ ለአራት አመታት የአለማችን ቁጥር አንድ ደስተኛ አገር ሆና መመዝገቧንም አስታውሷል፡፡
የመካከለኛው አፍሪካ ሪፐብሊክ ዜጎች ጥናቱ ከተሰራባቸው 155 የአለማችን አገራት ህዝቦች ሁሉ በኑሯቸው የማይደሰቱ ህዝቦች ናቸው፤ አገሪቱም በአመቱ የአለማችን አገራት የደስተኛነት ዝርዝር ውስጥ የመጨረሻውን ደረጃ ይዛለች ያለው ሪፖርቱ፤ ብሩንዲና ታንዛኒያ እንደ ቅደም ተከተላቸው ከመጨረሻ ሁለተኛና ሶስተኛ ደረጃ ላይ መቀመጣቸውን አመልክቷል፡፡
የአገር ውስጥ ጠቅላላ ምርትና የነፍስ ወከፍ ገቢ፣ አማካይ በህይወት የመኖር ጣራ፣ የህይወት ምርጫን የማድረግ ነጻነትና የመሳሰሉት ጉዳዮች የአገራቱን የደስተኛነት ደረጃ ለመገምገም በጥቅም ላይ ከዋሉ መስፈርቶች መካከል ይጠቀሳሉ ያለው ሪፖርቱ፤ ደስተኛነት ገንዘብ የመያዝና ያለመያዝ ጉዳይ አይደለም፤ ለዚህም አንዳንድ ሀብታም አገራት ዝቅ ያለ የደስተኝነት ደረጃ ይዘው መገኘታቸው ማረጋገጫ ነው ብሏል፡፡

 ድንገተኛ እሳት በሚፈጥረው ኖት 7 ምርቱ የከፋ ቀውስ ውስጥ ገብቶ የከረመው ሳምሰንግ ኩባንያ፣ አዲሱን ስማርት ፎን ምርቱን ጋላክሲ ኤስ 8ን በአንድ ወር ጊዜ ውስጥ ይፋ በማድረግ ለገበያ ያበቃል መባሉን ዘ ኢንዲፔንደንት ዘግቧል፡፡
ሳምሰንግ ኩባንያ በጉጉት ሲጠበቅ የነበረውንና ከዚህ ቀደም ለገበያ ከቀረቡት የጋላክሲ ስማርት ፎኖች የተለየ ይዞታና ገጽታ ይኖረዋል የተባለውን አዲሱን ምርቱን ጋላክሲ 8ን እስከ ሚያዝያ ወር መጨረሻ ለገበያ እንደሚያበቃ የሚጠቁሙ መረጃዎች መውጣታቸውን የጠቆመው ዘገባው፤ የመሸጫ ዋጋውም 799 ፓውንድ ይሆናል ተብሎ መገመቱን ገልጧል፡፡
ሳምሰንግ በጥቁር፣ በብርማ እና በሃምራዊ ቀለም እንደሚመረትና በካሜራ፣ በባትሪና በሌሎች ከዚህ ቀደም ከነበሩት ምርቶች የተለየ እንደሚሆን የተነገረለትን ይህን አዲስ የስማርት ፎን ምርቱን ለገበያ ለማብቃት ያቀደው ቀደም ብሎ ቢሆንም፣ በኖት 7 ምርቱ ሳቢያ የገባበት ቀውስ ዕቅዱን እንዲያራዝም እንዳስገደደው ዘገባው አስታውሷል፡፡
ኩባንያው ከጋላክሲ 8 በተጨማሪ ጋላክሲ 8 ፕላስ በሚል ስያሜ ያመረተውን አዲስ የስማርት ፎን ምርቱን ለገበያ ያበቃል መባሉን ያስታወቀው ዘ ኢንዲፔንደንት፤ የጋላክሲ 8 ፕላስ የመሸጫ ዋጋ ደግሞ 899 ፓውንድ ይደርሳል ተብሎ እንደሚገመት አብራርቷል፡፡

 የትንሳኤን በዓል ምክንያት በማድረግ በኢዮሃ አዲስ ኢንተርቴይመንትና ኤቨንት የተዘጋጀው  “ኢዮሃ ፋሲካ” ኤክስፖ ዛሬ ከቀኑ 8፡00 ጀምሮ በአዲስ አበባ ኤግዚቢሽን ማዕከል ይከፈታል፡፡
ኤክስፖው ሻጭና ገዢን ከማገናኘት ባለፈ ለ22 ቀናት የሙዚቃ ኮንሰርቶችን በወጣትና አንጋፋ ድምፃዊያን በማቅረብ የመዝናኛና የፌስቲቫል ድባብ እንዲኖረው መደረጉን የኢዮሃ አዲስ ኢንተርቴይመንትና ኤቨንት ዋና ሥራ አስኪያጅ ወ/ሮ አዩ አለሙ ገልፀዋል፡፡
ከ400 በላይ የውጭ፣ 8 የአገር ውስጥ የንግድ ድርጅቶች ይሳተፉበታል የተባለው ይሄው ኤክስፖ፤አራት እውቅ ባንዶች የሚሳተፉበትና ከ100 በላይ ታዋቂ ዘፋኞች የሚያቀነቅኑበት የሙዚቃ ኮንሰርት፣ በዝነኛ ዲጄዎች የሚቀርብ ሙዚቃ፣ ከ80 በላይ ወጣቶችን የሚያሳትፍ  ዘመናዊና ባህላዊ የዳንስ ውድድር እንደሚቀርብበት ተጠቁሟል፡፡  
የፋሲካ ኤክስፖውን በየቀኑ ከ30 ሺህ በላይ፣ በጠቅላላ ግማሽ ሚሊዮን ህዝብ ይጎበኘዋል ተብሎ እንደሚጠበቅ ዋና ሥራ አስኪያጁዋ ለአዲስ አድማስ ተናግረዋል፡፡  
 ኢዮሃ አዲስ ኢንተርቴይመንትና ኤቨንት፤ በየቀኑ ወደ ኤክስፖው የሚመጡ ጎብኚዎች የሚገቡበትን ትኬት ቁጥር ለሽልማት ወደ 86 በአጭር መልዕክት በመላክ መኪና፣ ሞተር ሳይክልና ሌሎች ሽልማቶችን የሚያገኙበትን ዘመናዊ አሰራር ማመቻቸቱም ተነግሯል፡፡ የዚህን ዓመት የገና ኤክስፖ ጨምሮ ያለፈውን ዓመት የገናና የፋሲካ ኤክስፖዎች ያዘጋጀው ኢዮሃ፤ የዘንድሮን የፋሲካ ኤክስፖ ጨረታ በ13.6 ሚሊዮን ብር ማሸነፉ ታውቋል፡፡

ሩሲያ ካፈራቻቸው ታላላቅ የሥነ ጽሑፍ ሰዎች ውስጥ ገጣሚና ተርጓሚ የሆነችው ማሪና ኢቫኖቫ ስቬታየቫ አንደኛዋ ናት፡፡ ማሪና ኢቫኖቫ ሳይንስና የኪነ ጥበብ ዕውቀት ከአላቸው ቤተሰቦች ሞስኮ ውስጥ የተወለደቺው እ.ኤ.አ መስከረም 26 ቀን 1892 ዓ.ም ነው፡፡
ያረፈችው ደግሞ እ.ኤ.አ በ1941 ዓ.ም ላይ ነው። አባቷ ኢቫን ብላዲሚሮቪች ስቬታየብ የሞስኮ ዩኒቨርስቲ ፕሮፌሰር፣ የታወቀ ፈላስፋ፣ ዲሬክተርና የኪነ ጥበብ ሙዚየም መሥራች (በአሁኑ ሰዓት በፑሽኪን ስም በሚጠራው ከተማ የሚገኘው ሙዚየም) ነበር፡፡
ወላጅ እናቷ እመት ማሪያ ኔ ሜንም የተለየ ዕውቀት የነበራትና የኮንሰርት ፒያኖ ተጫዋች ነበረች፡፡
ማሪና ሞስኮ ውስጥ የሁለተኛ ደረጃ ትምህርቷን የተማረቺው በግል ት/ቤት ነው። በልጅነቷ ቤተሰቧ የተለያየ ጉብኝት ለማድረግ ወደ ጀርመን፣ ስዊዘርላንድነሰ ወደ ሶርቦን ፓሪስ በሚሄድበት ወቅት አብራ በመሄድ ትምህርቷን ትከታተልና ቋንቋም ታጠና ነበር፡፡ እ.ኤ.አ በ1908 ደግሞ በራስዋ ፍላጎት ወደ ፈረንሳይ (ፓሪስ) ሄዳ ሶርቦን ውስጥ የጥንት ፈረንሳይኛ ሥነ ጽሑፍ ኮርስ መከታተል ጀመረች፡፡ በ16 ዓመቷ ግጥም መግጠም የጀመረቺው ስቤታየቫ፤ 18 ዓመት ሲሞላት ወደ ሩሲያ ተመልሳ የመጀመሪያዋ የሆነ የሥነ ግጥም ስብስብ መጽሐፍ ‹‹ የምሽት አልበም›› (EVENING ALBUM) በሚል ርዕስ አሳተመች። በኋላም ማለት እ.ኤ.አ በ1912፣በ1913፣በ1916 ዓ.ም የተጋጋለ ውስጣዊ ስሜቷንና የሩሲያን ነባራዊ ሁኔታ የሚያንፀባርቁ ሌሎች ሥራዎቿን ለህትት አበቃች፡፡ በተለይም “ከፍታ” የተሰኘው ግጥሟ ለሩሲያና ለሩሲያ ገጣሚዎች የተበረከተ ሲሆን ኩራትን፣ ጀግንነትን፣ የበለፀገ እውቀትንና ፍፃሜ የሌለው ስሜትን ያመለክታል፡፡
‹‹የምሽት አልበም›› የሚለው ግጥም ስለ ልጅነቷና ስለ ወጣትነቷ ዘመን ያትታል፡፡ ማስታወሻ አድርጋ ያበረከተችውም ለዚሁ ዘመኗ ነው፡፡
እ.ኤ.አ በ1912 ዓ.ም ማሪና ሰርጌይ ኢፎርን የተባለና የዛሩ መንግሥት ወታደር የነበረ ሰው አግብታ ሁለት ሴቶችንና አንድ ወንድ ልጅ ወልዳለች፡፡ የማሪና ሰቬተየቫ ሕይወት ከሩሲያ አብዮት ጋር የያያዘ ነበር፡፡ ባለቤቷ ኢፎርን ነጩ ጦር (the white guard) እየተባለ ከሚታወቀው የዛሩ መንግሥት ጦር ሰራዊት ጋር ተሰልፎ አብዮተኞችን/ ሶቭየቶችን ወይም ቦልሸቪኮችን/ ሲወጋ ነበር፡፡
ማሪና ‹‹ገርልፍሬንድ›› በሚለው ግጥሟ ተደንቃና ተመስጣ ገጣሚና የኦፔራ ቲአትር ባለሙያ ከሆነችው ከሶፍያ ፓሞክ ጋር ተዋወቀች። ምክንያቱም ሶፍያ ፓሞክ በወቅቱ በዚህ ግጥሟ ዝናን አትርፋ ነበር፡፡ ቀጥላም በዛሩ ዘመነ መንግሥት የቀይ ጦር ሽምቅ ታዋጊ ወታደር ከነበረና ኮንስታንቲን ፎዜቪች ከተባለ ገጣሚ ጋር ትውውቅ አደረገች፡፡ ኮንስታንቲን ‹‹የተራራ ግጥሞች›› እና ‹‹ የመጨረሻ ግጥሞች›› የተሰኙ ሥራዎች ስለነበሩት እነዚህን አንብባ አድናቆቷን ገለጸለችለት፡፡
እ.ኤ.አ በ1917 የኦክቶቨር ሪቮሉሽን ወቅት ተይዛ ለ5 ዓመት ታሥራለች፡፡ ከአብዮቱ ጋር በተያያዘ በተከታታዮቹ ዓመታት ድርቅና ረሀብ በሩሲያ በተከሰተበት ወቅት አንደኛዋ ሴት ልጇ በረሀብ ምክንያት ሞታበታለች፡፡
እ.ኤ.አ በ1922 ዓ.ም ማሪና ባለቤቷንና ቤተሰቧን ይዛ ወደ በርሊን፣ ከዚያም ወደ ፕራግ፣ ቀጥላ በ1925 ወደ ፓሪስ ተሰደደች፡፡ በፓሪስ የሩሲያ ማኅበረሰብ አባላት ጋርም መኖር ጀመረች። ነገር ግን አብዛኞቹ ስደተኞች የቀድሞው የዛር መንግሥት ወታደሮች ስለነበሩ የማሪና ባለቤት ሰርጌይ ኢፎርን የቦልሸቪኮች ሰላይ ሳይሆን አይቀርም ብለው ስለገመቱ እርሱን መፍራት ጀመሩ፡፡ በኋላም ነገሩ እውነት ሆኖ ተገኘ፡፡ ከጊዜ በኋላ ሰርጌይ ኢፎርን ወደ ሩሲያ ተመለሰ፡፡ ሞስኮ እንደደረሰም ታሥሮ ከቆየ በኋላ ተገደለ፡፡ ማሪና በስደት ዘመኗ ወጎችንና የትረካ ሥራዎችን ደርሳ ለማሳተም ችላለች፡፡ የአብዛኞቹ ግጥሞቿ ጭብጥ የሚነሳው ከአፈ-ታሪክና ከኅብረ ዝማሬ ሲሆን የአገጣጠም ስልቱ ደግሞ በታላቁ ሩሲያዊ ገጣሚ በአሌክሳንደር ብሎክና በታላቂቱ የኪነ ጥበብ ሰው በአና አህማቶቫ የአጻጻፍ ቴክኒክ የተቃኘ ነው፡፡ በሥራዎቿ ውስጥ የሩሲያ ኦርቶዶክስ ሃይማኖትና ጸሎተኞች፣ የእምነት ዕሴቶች ከዘመናዊ አስተሳሰብ ጋር ተቃኝተው ይታያሉ፡፡
ማሪና ከብዙ ነገር ተገልላና ብቸኛ ሆኖ በስደት ብትቀመጥም የነፍስ ጥሪዋን ግን አልረሳችም። በከፍተኛ ስሜት ተነሳስታ ብዙ የጻፈችው በስደት ጊዜዋ ነው፡፡ ‹‹መለያየት››፣ ‹‹ንግድ››፣ ‹‹ሥነ ልቡና››፣ ‹‹ከሩሲያ በኋላ››፣ ‹‹ይድረስ ለልጄ››፣ ‹‹የአገር ናፍቆት››፣ ‹‹ቼቺያ›› /በወቅቱ ፖለቲካ ላይ የሚያተኩር ሥራ / የተባሉትን ሥራዎች ደርሳ ያሳተመቻቸው በስደት ዘመኗ ነው፡፡ ከማሪና ታላላቅ የግጥምና የልቦለድ ሥራዎች ውስጥ
በፖሪስ ውስጥ፣ ጸሎተኛው፣ ለእናቴ፣ ስብሰባ፣ ኒና ይቅርታ አድርጊልኝ … የሚሉት ይጠቀሳሉ፡፡
ማሪና እ.ኤ.አ ከ1939 ዓ.ም ጀምራ ወደ ሀገሯ በመመለስ ሞስኮ ውስጥ ለመኖር ብትፈልግም በፖለቲካ አመለካከቷ ምክንያት የሥነ ጽሑፍ አፍቃርያንና በማኅበረሰቡ ዘንድ የተገለለች ሆነች። ከዚህም የተነሣ እ.ኤ.አ በ1941 ዓ.ም ራስዋን አጥፍታለች፡፡
ታላቁ ገጣሚ ቦሪስ ፖስተርናህ አሟሟቷን አስመልክቶ ሲናገር፡-
‹‹ማሪናን ቀደም ብሎ የሥነ ጽሑፍ ቢሮክራቶች ልበቢስ በሆነ መንገድ ባይቀርቧት ኖር ራስዋን አታጠፋም ነበር›› ብሏል፡፡
የጽሑፍ ሥራዎቿ የሰላ አእምሮ፣ በጥልቀት የሚያይ ዐይንና አስተዋይ ልቡና የነበራት ታላቅ ሴት የነበረች መሆኗን አስመስክረዋል፡፡
በ20ኛው ክፍለ ዘመን በወጥነት ከቀረቡት የግጥም ሥራዎች ውስጥ የማሪና ስቤታየቫ በዋነኛነት ይጠቀሳል፡፡ የእርስዋ የሥነ ግጥም ምንጭ የፈለቀው ተቃርኖ ከበዛበት የግል ሕይወቷ ነው፡፡ የቋንቋ አጠቃቀሟ የተመጠነ፣ በጥቂት ቃላት ብዙ የምትናገርነ ገጣሚ ናት፡፡ በጭብጥ ረገድ ካነሳቻቸው በርካታ ርእሰ ጉዳዮች ውስጥ የሚበዛው ሴታዊነት፣ ወሲብ፣ የሴቶች ግላዊ ሕይወትና በማኅበራዊ ኑሮ ስለአላቸው ሚና ነው፡፡
ለማሪና ስቬታየቫ በአሁኑ ሰዓት የሩሲያ መንግሥት በመኖሪያዋ አካባቢ በሚገኘውና ቦሪስግሌቭስኪ ተብሎ በሚጠራው ሠፈር ሐውልት አቁሞላታል፡፡