Administrator

Administrator

የሥዕል ትርዒት ዳሰሳ
(Exhibition Review)
የትርዒቱ ርዕስ፡
የኢትዮጵያ ዓመታዊ የሥነ-ጥበብ ፌስቲቫል
የትርዒቱ አይነት፡
ፌስቲቫል
የሚታይበት ጊዜ፡
ሰኔ 18 - 27: 2008 ዓ.ም
ቦታ፡
በኦሮሞ ባሕል ማዕከል
ዳሰሳ አቅራቢ፡
ሚፍታ ዘለቀ(የሥነ-ጥበብ አጋፋሪ)


የኢትዮጵያ ዓመታዊ የሥነ-ጥበብ ፌስቲቫል
ወሳኝነት ያላቸው የግል ትርዒቶች ያውም በሀገራችንም ሆነ በዓለማችን የሥነ-ጥበብ እንቅስቃሴ ጉልህ ሚና እየተጫወቱ ያሉ ሁለት ሰዓልያን ስራቸውን በመዲናችን በሚያሳዩበት ሳምንት ዳሰሳውን ቢያንስ ከሁለት አንዳቸው ላይ መስራት ሲኖርብኝ፣ ወደ ፌስቲቫል ዳሰሳ ማተኮሬ፣ ይህ የተጠቀሰው ፌስቲቫል ዓመታዊ በመሆኑና አመቱን ጠብቆ ሲመጣ (በዚህ ሁኔታው ጭራሽ ባይመጣ እላለሁ) ከነ ህፀፁና ግሳንገሱ ተመልሶ እንዳይመጣ ትምህርትና ተግሳጽ ቢወስድ ከሚልና አዘጋጁ የኢትዮጵያ ሠዓሊያንና ቀራጽያን ማህበር ባለፉት ዓመታት ውስጥ ካለው እንቅስቃሴ አንፃር እየተጫወተ ወይም እያልተጫወተና እየቀለደባቸው ካሉ የማህበሩ ማንነትንና ህልውና ጥያቄ ውስጥ ከሚከቱ ሁነቶች አኳያ ሊነሱ የሚችሉ ነጥቦችን በመተንተን የዛሬውን ዳሰሳ እነሆ፡፡
(ለሚቀጥሉት ሳምንታት ዳሰሳዎች የተሻለ አትኩሮት እንዲኖራችሁ ትርዒቶቹን ብትመለከቱ ጠቃሚ ይሆናል፡፡ በአዲስ ፍይን አርት - ሠዓሊ መሪኮከብ ብርሃኑ የግል ትርዒት፣ በሞደርን አርት ሙዚየም ገብረክርስቶስ ደስታ ሴንተር - ሠዓሊ ጁሊ ምሕረቱ ስራዎቻቸውን በማቅረብ ላይ ይገኛሉ፡፡ ለአቅጣጫ +251 911 702 953)
“የኢትዮጵያ”
“ልጅሽ ነኝ፤ አንቺም እናቴ ነሽ” በሚል የፍቅር አይሉት የድፈረት ወይ የንቀት ካባ የተጀቦነች ብሔርተኝነት (Nationalism) የምታመጣው ጣጣና እንክርፍፍነት ቀላል እንዳይመስላችሁ፡፡ ”የጋን ውስጥ መብራት” ከሆነና ውጪው አረፋ ከሞላው ውሃ ተነክሮ ከሚወጣና እፍ ሲሉት የሚያምር ቀለማትን አየር ላይ ለሽራፊ ሰከንዳት በተንሳፋፊ ክቦች አሳይቶ ከሚጠፋው (bubble) እንኳ የማይተካከል ሃሳብ ይዞ፣ስያሜውን ግን ጠጣር በሆነ ውህዷ ከምትታወቀው /ቢያንስ ውስጣችን እንዲህ ዓይነት ግዝፈት ካላት/ ሀገራችን ስም በመነሳት “የኢትዮጵያ …” እያሉ ስያሜ መስጠት አይሉት ማላዘን የተለመደና ብዙ ተቋማት ለሚወጥኑት የእንቶ-ፈንቶ ድግስ ማድመቂያ ተቀጽላ ከማድረግ አልፎ ነቀርሳ እየሆነ መጥቷል፡፡ ምናለ በሆነ ባልሆነው ጨርቋን ባይጎትቷት፣ምናለ ባይጎነትሏትና ባይተነኩሷት? “ምነው?” የማትል ድንዙዝ ከሆነች ሰነባብታለች፡፡ ለነገሩ እሷም አውቃ የተኛች ይመስላል፤እንኳን ሲጠሯት ጆሮዋን ሲቆርጧትም ማነው የማትል ድንዙዝ ከሆነች ሰነባብታለች፡፡
ለነገሩ ለምን “የኢትዮጵያ” አልክ ብሎ የሚጠይቅ እስከሌለ ድረስ ‘ሃገር የጋራ ናት’ በሚለው አባባል፣ በመደፋፈር ጨርቅ ጉተታና ጉንተላ አይደለም ‘የአስገድዶ መድፈር’ ቢደርስባት እንኳን የሚገርም አይሆንም (ሀገር ፆታ የለውም፣ የአንድ ሀገር ስያሜም ወንዴና ሴቴ የለውም፡፡ እዚህ ፅሁፍ ላይ ሀገሬን አንቺ ብላትና በሴት ፆታ ብጠራት የቀለለኝና የተመቸኝ በመሆኑ እንጂ ፆታ እሱ ወይም ‘እሷ ኢትዮጵያችን’ እያልኩ ብጠራው ፆታዊ ከሆነ ከተግባራዊ ጉንተላ፣ ከሱሪ ጉተታና መደፈር ላያመልጥ የሚችል ሀገራዊ ማንነት ላይ የቆምን ባለመሆኑ ኢትዮጵያን እሱ አንተ ብንለው ወይ እንደለመድነው አንቺ- እሷ ብንላት ምንም ለውጥ እንደሌለው ለፆታዊ (gender) ጉዳዮች ስሱ የሆነ/ነች አንባቢ እንደሚረዳኝ /ትረዳኝ ተስፋ አደርጋለሁ፡፡ )
እና … ‘የኢትዮጵያ’ በሚል ስያሜዎችን ከሚጠቀሙት ዝግጅቶችና ተቋማት መሀከል የኢትዮጵያ ሠዓሊያንና ቀራፂያን ማህበር፣ ከኢ.ፌ.ዲ.ሪ ባሕልና ቱሪዝም ሚኒስቴር ጋር በመተባበር በየዓመቱ የሚያዘጋጀው ይህ ስሙ ብቻ የከበደውና የተካበደው ዓመታዊ ፌስቲቫል አንዱ ነው፡፡ እስቲ ውስጡ ይፈተሽ፡-
የኢትዮጵያ ዓመታዊ የሥነ-ጥበብ ፌስቲቫል ማንን ነው የሚወክለው? ‘የኢትዮጵያ ሠዓልያንን’፤ ‘የኢትዮጵያ ዘመንኛ ሥነ-ጥበብን?’ ‘የኢትዮጵያ ብሔር ብሔረሰቦች ሥነ-ጥበባዊ ተዋፅኦን’… የቱ ጋ ነው የፌስቲቫሉ “የኢትዮጵያዊ”ነት?፡፡“የኢትዮጵያ” የምትባለው ኢትዮጵያ በሌለችበት ምነው ስሟን ማንቆለጳጰስ ብቻ ተወደደ? ነው ወይስ የኢትዮጵያ ስለተባለች ብቻ ሆ…! ብሎ የሚነሳ ሥነ-ጥበብ አለ …? “የኢትዮጵያ” ስለተባለች ብቻ ደስ የምናሰኛት ኢትዮጵያ አለች?…. ካለችም ምናለ ኢትዮጵያነቷን የሚወክል ሥራ ሰርተንላት ስያሜዋን ጥቅም ላይ ብናውለውና ደስ ብናሰኛት… አለዚያ አርፈን ብንቀመጥና እሷም ባለችበት አርፋ ብትቀመጥ- ባንነነዘንዛት ነው የሚሻላት፡፡ ስሟ በተጠራ ቁጥር ስቅ እያላት ተቸገርች እኮ!
… ፌስቲቫሉ “የኢትዮጵያዊ”ነት ራዕይ ከሌለው፣ለማይወክላት ስራ የማይወክላትን ስያሜ እየሰጠ ችክ አይበልባት … የኢትዮጵያ ዓመታዊ የሥነ-ጥበብ ፌስቲቫል አንዱና ዋንኛው ችኮ በመሆኑ እተቸዋለሁ! (ማለት የተቻለበት በምክንያት ከቀረበልኝም ሂሴን ለመዋጥ ዝግጁ ነኝ!)
የማዝነው - ይልቅስ የማዝነው በስራዎቻቸው “ኢትዮጵያን” በብቃት የመወከል ሥነ-ጥበባዊ አቅምና ህልውና ያላቸው ጉምቱ የሥነ-ጥበብ ሰዎቻችን ኢትዮጵያችንን ለማይወክላት የሥነ-ጥበብ ፌስቲቫል “የኢትዮጵያን” ታላቅነት (glory) ለማጉላትና ለማድመቅ (ሊሆን ይችላል) ወይም በቅን ልቦና ጊዜአቸውንና ስማቸውን መጠቀሚያ ማድረጋቸው ወይም መጠቀሚያ እንዲሆን መፍቀዳቸው፡፡ ጊዜአቸውና ስማቸው ብክነት ላይ መዋሉን ልብ ባለማለታቸው ግን አዝናለሁ፡፡ ፌስቲቫሉ ከዓመት ወደ ዓመት እያሽቆለቆለ ሲመጣ እያዩ፣“የኢትዮጵያ” የሚለውን ስያሜ መጠቀሙን ባይጠይቁና፣ ተው ብለው ባይገስፁ እንኳ ፌስቲቫሉ እንዲሻሻል ያደረጉት አስተዋፅዖ መኖር አለበት እላለሁ፡፡ (ካለም … ይኸው ባደባባይ ነው የምናገረው … ባደባባይ እማራለሁ እታረማለሁ፡፡) ሆድ ያባውን በጋዜጣ ያወጣዋል እንዲሉ የእኔን ነጥቦች እንካችሁ፡-
የፌስቲቫሉ አጀማመርና ከፍታ (ከፍታ ከተባለ)፡ የ2006 ዓ.ም የመጀመሪያው ሩብ የበጀት ዓመት አካባቢ ከባሕልና ቱሪዝም ሚኒስቴር ጋር በመተባበር የኢትዮጵያ ሠዓሊያንና ቀራፂያን ማህበር፣ ለሠዓሊያንና ለሥነ-ጥበብ ተቋማት ጥሪ አደረገ፡፡ በጥሪው መሰረት ተከታታይነት ያላቸው ረዘም ያለ ጊዜ የፈጁ ውይይቶች  ተካሄዱ፡፡ የውይይቱ ጭማቂ ይህን ፌስቲቫል ወለደ፡፡ “በኢትዮጵያ የሥነ-ጥበብ ታሪክ ውስጥ እንዲህ ያለ ክብር፣ ለሠዓሊያንና ለሥነ-ጥበብ ሲሰጥ ያየሁት በዚህ ነው .. መቼስ ምን እላለሁ አንግሳችሁናል!”  የሚል ለሙያው ጥልቅ ፍቅር ያለው ሠዓሊ ከሰጠው አስተያየት ጀምሮ፣ ከጥሪው በኋላ ባሉ ስብሰባዎችና በፌስቲቫሉ አካሄድና አሰራር  ዙሪያ ጥርጣሬዎቻቸውና ጥያቄዎቻቸው በማህበሩም ሆነ በሚኒስቴሩ ሊፈታ ባለመቻሉ አንዳንዳቸው እቅጩን ተናግረው ፣ ሌሎች አጉረምርመው፣ሌሎች በዝምታ ተለጉመው ቀስ በቀስ ድምፃቸውን አጠፉ፡፡ ከጥሪውም ከፌስቲቫሉም ቀሩ፡፡ ሃሳቡ ቀጠለ፡፡ “ጥበብ ለሁሉም!” በሚል መሪ ቃልም ዝግጅቱ ተጀመረ፡፡
ሚኒስቴሩ በፌስቲቫሉ እንዲተገበሩ በቀረቡ ሃሳቦች ምንነት ላይ ትኩረት ከመስጠት ይልቅ “በጀቱን ቀንሱ” እያለ የሥራ ዕቅዱን ሲያመላልስ በበጎ ፈቃደኝነት ሥነ -ጥበባዊ ፋይዳ ለመከሰት፣ ሃገራዊ ሃላፊነታቸውን ለመወጣትና ለመሳተፍ የመጡ ባለሙያዎችን ሲያጉላላ ቆይቶ፣ በሶስተኛው ሩብ የበጀት ዓመት መባቻ ላይ በሰኔ 2006 ዓ.ም የመጀመሪያው ፌስቲቫል ተከወነ፡፡
እንደ መጀመሪያነቱ እንዲሁም ቀጥለው ከመጡት ሁለቱ ፌስቲቫሎች አንፃር የዚህ ፌስቲቫል ከፍታ ልንል የምንችላቸውን ሥነ-ጥበባዊ ክዋኔዎችና ፕሮራሞችን እንጥቀስ፡፡ ከፍ ያለው በጣይቱ ኢንተርናሽናል አርት ሴንቴር በዋናነትም በወቅቱ የሴንተሩ አጋፋሪ ዘላለም ግዛው (ሠዓሊ) የተዘጋጀውና የተከወነው የሕፃናትና የጎዳና ላይ ታዳጊዎች የሥዕል ሰርቶ ማሳያ (workshop) እና የሰርቶ ማሳያው የሥዕል ትርዒት ነው፡፡ የኢትዮጵያ ሴት ሠዓልያን ማኅበር በብሔራዊ ቴአትር ጋለሪ ያዘጋጀውና በጋለሪው በር የሚያልፍ ማንኛውንም ሰው ሥዕል እንዲስል የሚጋብዝ አሳታፊ መሰናዶ የመጀመሪያው ፌስቲቫል ከፍታ ሊባል ይችላል፡፡  ሌላኛው በጉራምዓይኔ የሥነ-ጥበብ ማዕከል የተዘጋጀውና አስር ሰዓልያንን አሳትፎ፣ ከጊዜ ወደ ጊዜ በመልሶ ማልማት ፍርስርሷ እየወጣና ማንነቷን እየተነጠቀች ከመጣቸው አዲስ አበባችን ውስጥ ካሉ አካባቢዎች በንፅፅር ሲታይ በዚያን ጊዜ (2006 ዓ.ም) እና አሁንም በጥቂቱ( ታሪካዊው ውቤ በርሃ መንኮታኮት ውጪ) የታሪካዊነት ቅሪታቸው ሊታይ በሚችሉት በአራት ኪሎና የፒያሳ አዋሳኝ መሃል ያሉ ታሪካዊ ቤቶችና መንገዶች፣ ምልክት የሆኑ ቦታዎች (landmarks)፣ መነጋገሪያ የሆኑ ቦታዎችን እንዲሁም እየተገነቡና እየፈረሱ ያሉ የፒያሳና የአራት ኪሎ ቦታዎችን የሚቃኙ ሥዕሎች ተሰርተዋል፡፡
ይህም ቦታዎቹን በሥነ- ጥበብ ከመሰነዱም በላይ ሰዓልያኑ በቦታዎቹ ላይ ቆመው ሲስሉ በተለያዩ የሬዲዮን ጣቢያዎች በቀጥታ ይተላለፉ ስለነበር ክዋኔውን በሬዲዮን የሰሙና ቦታው ሲመላለሱ የነበሩ መንገደኞች፣ቆም ብለው ሠዓሊያኑ የሚሠሩትን የማየትና የመጠየቅ፣በዚያውም (አባይን በጭልፋ አይነት ቢሆንም) ስለ ሥነ-ጥበብ ያላቸውን ግንዛቤ የማዳበር እድል የከፈተ ክዋኔ ነበር፡፡ በሐበሻ ስቱዲዮው ሠዓሊ ወርቅነህ በዙ የቀረበውና በከተማዋ ዋና ዋና ቦታዎች እየተዘዋወረ የታየው የፓፔት ትርዒት፣የሥነ-ጥበብን ሰፊ ተደራሽነትና ተግባራዊ ፋይዳ ያመላከተ ነበር፡፡ የትርዒቱ አካል የነበረውና በሁለት ዓመት ውስጥ ካቀረባቸው ሠዓሊያንና ትርዒቶች መሀከል ስራዎችን መርጦ ካሳየው ጋለሪያ ቶሞካና የታላላቅ ሠዓልያንን ስራዎች ከወጣት ሠዓልያን ስራዎች ጋር አጣምሮ በትርዒት መልክ ካሳየው የላፍቶ አርት ጋለሪ በተጨማሪም ያልተሳካ የፓናል ውይይትም ተወጥኖ ነበር፡፡ በዚህ በመጀመሪያው ፌስቲቫል ከሚኒስቴር መ/ቤቱ የአንዱ ዳይሬክቶሬት ቢሮ ሃላፊ ከሆኑ ተወካይ፣ በአንድ የትርዒት መክፈቻ ላይ ብቅ ከማለት ውጪ የሚ/ር መ/ቤቱ ባለስልጣናት ዝር አለማለታቸው፣ ለፌስቲቫሉ የሰጡትን ዝቅተኛ ትኩረት ያሳየ ነበር፡፡
ሁለተኛው ፌስቲቫል ከሞላ ጉደል በቀደሙት ፌስቲቫሎች የነበረውን ችግር ለመቅረፍና አዲስ አካሄድ ለመቀየስ ያለመ ነበር፡፡ ይበልጥ አልተሳካለትም እንጂ፡፡ የተሻለ በጀት መድቦ ነበር፤ወደ ሰባ በመቶ ተመላሽ ሆነ እንጂ፡፡ ተሳታፊ ሰዓሊያንና ተቋማት ብቁ ሀሳብ ይዘው አልመጡም እንጂ፡፡ የሚ/ር መ/ቤቱ ባለስልጣናት ሲገኙ፣ትርዒቱ የተመልካች ድርቅ መታው እንጂ (በኢትዮጵያ ባህል ማዕከል (ስብሰባ ማዕከል) ነበር የተዘጋጀው፡፡)
የዘንድሮውና ሶስተኛው የኢትዮጵያ ዓመታዊ የሥነ-ጥበብ ፌስቲቫል ደግሞ ይበልጥ ግራ የገባው፣የተደናበረ አቅጣጫውን የሳተ ሆኖ አልፏል፡፡ ይህ ፌስቲቫል ያስተናገደውንና በሶስቱ ፌስቲቫሎች የተስተዋሉ ቁልቁለቶችን በመዘርዘር ትችቴን አጠናቅቃለሁ፡፡
የፌስቲቫሉ ቁልቁለቶች
የወጥነት ጉድለት፡- የኢትዮጵያ ዓመታዊ የሥነ-ጥበብ ፌስቲቫል ሶስቱንም ጊዜ መልክ የሌለው፣ የተዘባረቀ፣መያዣ የጠፋውና ቅርጽ አልባነቱን ያሳየ ፌስቲቫል ሲሆን በዚሁ ለአራተኛና ከዚያም ለዘለለ ጊዜ ከቀጠለ ይህ አሜባዊ ቅርፅ-አልባነቱ ወደ ሙሉ ጥፋትነት ይቀየራል ባይ ነኝ፡፡ ስለዚህ ወጥ ቅርፅ (FORMAT) ይዞ መምጣት ይጠበቅበታል፡፡ በዓለም ላይ ያሉ ስኬታማ ፌስቲቫሎች ይህን ነው ሚያደርጉት፡፡
ቅንድብ እንኳ መሆን አለመቻል፡- ለሶስተኛ ጊዜ የተደገሰ፣ “የኢትዮጵያ” የሚል ትልቅ መጠሪያ ያነገበ፣ በማህበር ኃላፊነትም ሆነ በማህበሩ የበላይ ጠባቂነት በሙያቸው ከበቂ በላይ ልምድ ኖሯቸው እየሰሩ ያሉና እየጠበቁ ያሉ ሠዓሊያንና ሙያተኞችን በስሩ ካቀፈ፣ በሚኒስቴር መ/ቤት ድጋፍ ካለውና… ሌሎች አቅሞችን ማዳበር ከሚችል ፌስቲቫልነቱ አንፃር ሲታይ እንኳን ዓይን ይቅርና ቅንድብ መሆነ አለመቻሉ የፌስቲቫሉ ሌላኛው ቁልቁለት ነው፡፡
3- የተመልካች ትኩረት፡-ፌስቲቫሉ እንደ አብዛኛዎቹ የሃገራችን የሥነ-ጥበብ ተቋማት ሁሉ በእርግጠኝነት ሊገነባ የሚሻው የተመልካች አይነት ላይ ትኩረት አላደረገም፡፡ “የኢትዮጵያ” ይላል፡፡ ትኩረቱ የኢትዮጵያ ህዘብ ላይ ነው? የአዲስ አበባ? የሥነ-ጥበብ ማህበረሰቡ? ተማሪው? ወጣቱ? ነጋዴው? የትኛውም ላይ ትኩረት ያለው አይመስልም፡፡ ለህዝቡ ማድረስም ጉዳዩ አይመስልም፡፡ “ጥበብ ለሁሉም!” በሚል መሪ ቃል ነው ሶስቱም ጊዜ የተከወነው፡፡ ጥበብ ለሁሉም ምን ይሁን? ብለን ስንጠይቅ ግን “አይድረስ! ፤ ለሁሉም ቢደርስም ባይደርስም መከወኑ አይቀርም … ዘንድሮ 3ኛው ነው እሺ!” የሚሉና ወዘተ ምላሾችን የሚሰጥ የሚመስል የተመልካች ትኩረቱን ያልወሰነ ቁልቁለትም እየወረደ ነው፡፡
ተሳታፊያንና የስራዎቻቸው ውክልና፡- የትኛው የኢትዮጵያ ሠዓሊያንን ትውልድ ወይም የአሰራር ዘዬ ወይ የኪነ-ቁስ አይነት መሰረት በማድረግ ነው ፌስቲቫሉ ተሳታፊያንና ስራዎቻቸውን የሚመርጠው? ወጥ ወይም ግልፅ  የሆነ ቅርፅ የለውም፡፡ ወሰኑን የማበጀት ግዴታ ባይኖርበትም መግለፅና መተንተን ቢችል ግን የተሻለ ስራ ይሰራል፡፡ “የኢትዮጵያ” … እየተባለ በተሳታፊያንና በስራዎቻቸው የምትወከል ኢትዮጵያ አለመኖሯ .. ይህች ኢትዮጵያ በፌስቲቫሉ የመንፈስነት (ghost’ነት) ቦታ እንኳ እንደሌላት ያሳየናል፡፡
 ቸልታዎች፡- ሚንስትር መ/ቤቱ የፌስቲቫሉን አቋምም ሆነ አካሄድ ልብ ያለው አይመስለኝም፡፡ ወይም ረክቶበታል፡፡ አሊያም ምንም ይሁን ምን  … ዝም ብሎ መኖሩና መካሄዱ ብቻ ይበቃል የሚል ይመስላል፡፡ ከዘንድሮ መጪው ዓመት ይሻላል እያለ ሊሆን ይችላል፡፡ ከኢትዮጵያ ግብር ከፋይ ዜጎች ከሚሰበሰብ ገንዘብ ተቀንሶ እንዲሁም መንግስት ተበድሮና ተለቅቶ ከሚያመጣው ዓመታዊ በጀት ተቆንጥሮ በሚለቀቅ ፈሰስ የሚከወነው ፌስቲቫል፤ በመንግስት ሊቸረው ከሚገባው ትኩረት አንፃር ገና አፍላ ለሆነው የሥነ-ጥበብ ዘርፍ ፌስቲቫሉ ሊፈጥር የሚችለውን አቅም ሚኒስቴር መ/ቤቱ (እንደ ዋና የሥራ ሂደቱነት ማህበሩ)፣ ተሳታፊ ሰዓልያንና የሥነ- ጥበብ ተቋማት፣ ኢ-ተሳታፊ ሠዓሊያንና ተቋማት፣ የሥነ-ጥበብ ባለሙያዎችና አድናቂዎች እንዲሁም ሌሎች
ታዛቢያን (መቼም ታዛቢ አይጠፋም) ያሳዩት፣ እያሳዩ ያሉትና ወደ ፊት ሊያሳዩ የሚችሉት ቸልታዎች ፌስቲቫሉን ከቁልቁለት ወደ አዘቅት ሊጨምሩት ይችላሉ፡፡
ፌስቲቫሉ በአግባቡ ከተሰራበት ሊፈጥር የሚችለውን አቅም የሚጠረጠር ያለ አይመስለኝም፡፡ ለአብነት አንድ  ምሳሌ ልጥቀስ፡፡
ከ2000- አሁን -አዲስ ፎቶ ፌስት፡- ደስታ ፎር አፍሪካ (DFA Plc) በዋነኝነትም በፌስቲቫሉ የሥነ-ጥበብ አጋፋሪ፣በፎቶግራፈር አይዳ ሙሉነህ አማካኝነት የሚካሄደው አዲስ ፎቶ ፌስት መመለስ የሚገባው ጥያቄዎች ቢኖሩትም በስኬት እየተጓዘና በአንድ ግለሰብ ማለትም በአይዳ ሙሉነህ ጉንዳናዊ ትጋትና እልህ አስጨራሽ ጥረቶች እየተካሄደ ይገኛል፡፡ ዘመንኛ የኢትዮጵያ ሥነ-ጥበብም በዓለም ዓቀፍ መድረኮች ብቅ እንዲል ምክንያት የሆነ ፌስቲቫልም ነው፡፡ ዋቢ ባይሆንም መማሪያ ይሆናል፡፡
በ1987 ዓ.ም አዲስ አበባን የነቀነቀ፣ ሥነ-ጥበባችንን ያነቃቃ አንድ ፌስቲቫል ተካሄዷል፡፡ ለጊዜው ዝርዝር መረጃው የለኝም፡፡ ጥናት ቢደረግበት ግን አብነት መሆን የሚችል ፌስቲቫል ነበር፡፡
ጥቂት ስለ የኢትዮጵያ ሠዓሊያንና ቀራፂያን ማህበር፡
በ25 አባላት በበጎ አድራጎትና ማህበራት ማደራጃ ኤጀንሲ አዋጅ መሰረት፤ ግንቦት 2003 ዓ.ም ተቋቋመ፡፡ በአሁኑ ወቅት ከ200 በላይ አባላት አሉት፡፡ ሲያደርጋቸው ከቆዩ አንቅስቃሴዎች መሃል የተለያዩ የፓናል ውይይቶችን ማዘጋጀት፤ በአዳማ፣በመቀሌና በሐዋሳ መሰል ማህበራትን ማቋቋም፤ ለአባል ሠዓልያን ድጋፍ መስጠት  ለስራዎችቸው የመሸጫ መድረኮች ማመቻቸት፣የድጋፍ ደብዳቤ መፃፍ፤ ታላቁ የሕዳሴ ግድብ ግንባታ ጥበባዊ ደጀን እንዲኖረው፣በተለያዩ ጊዜያት ሠዓሊያንን ወደ ቦታው መውሰድ፤ ከጉብኝታቸው መልስ የተሰማቸውን እንዲስሉና የሣሉትን ሥዕል ለዕይታ ማቅረብ-----ጥቂቶቹ ናቸው፡፡
ማህበሩ ህፀፅ በሞላው መልኩ ከፈፀማቸው ወይም ከሚፈፅማቸው እንቅስቃሴዎች መሃል ይህ ዓመታዊ ፌስቲቫል እንዲሁም በቦሌ መንገድ አፍሪካ ጎዳና ላይ ባሉ የመንገድ አካፋይ የሲሚንቶ ግድግዳዎች ላይ አንድ ሥነ-ጥበብን በሀገር ደረጃ ለማንቀሳቀስ ከተመሰረተ ማህበር በማይጠበቅ፣ ሃላፊነት በጎደለው መልኩ ገና ካሁኑ በወራት ውስጥ ቀለሙ እየተፈገፈገ የመጣው፣የዕይታ ብክለት ያስከተለ፤ የኢትዮጵያ ሠዓሊያንን ሙያዊ ብቃት ጥላሸት የሚቀባ፣ የህዝብ ቦታንና በቦታው የሚተላለፈውን መንገደኛ እይታ የሚበክል----ቀለም መቀባት አይሉት ሥዕል መስራት ሊገለፅ የማይችል ተግባር ማከናወኑ ሌላኛው ህጸጹ ነው፡፡ በእርግጠኝነት ሌላ ጊዜ እመለስበታለሁ!
ቸር እንሰንብት !



የኢንዶኔዢያ ህጻናት የውፍረትም፣ የመቀንጨርም ተጠቂዎች ናቸው

   አራያ ፔርማን የተባለውና 192 ኪሎ ግራም ክብደት ያለው ኢንዶኔዢያዊ ታዳጊ በአለማችን በክብደቱ አቻ የማይገኝለት እጅግ ወፍራሙ ልጅ መባሉን ዘ ኢንዲያን ኤክስፕረስ ዘገበ፡፡
የ10 አመት ዕድሜ ያለው ፔርማን፤ክብደቱን ተቋቁሞ ቆሞ መንቀሳቀስ ባለመቻሉ ሳቢያ ትምህርቱን አቋርጦ ቤት እንደሚውል የጠቆመው ዘገባው፤ ወላጆቹ ልጁን በአግባቡ ለማሳደግ መቸገራቸውንና በልኩ የተሰፋ ልብስ ከገበያ ላይ በማጣታቸው ጨርቅ እያለበሱት እንደሆነ ገልጧል፡፡
በቀን አምስት ጊዜ ያህል እጅግ ብዙ መጠን ያለው ምግብ የሚመገበው ታዳጊው፤ክብደቱ ከጊዜ ወደ ጊዜ እየጨመረ መምጣቱ የዕለት ከዕለት ህይወቱን አስቸጋሪ እያደረገበት በመሆኑ፣ ወላጆቹ ለልጆቻቸው የሚሰጡትን የምግብ መጠን ለመቀነስ መገደዳቸውንም አስረድቷል፡፡የስምንት አመት ዕድሜ ሳለ ክብደቱ በፍጥነት መጨመር የጀመረውና የምግብ ፍጆታው እጅግ እያደገ የመጣው ታዳጊው፣ በአንዴ የሚመገበው ምግብ፣በአዋቂ እድሜ ላይ ለሚገኙ ሁለት ሰዎች የሚበቃ እንደሆነም ተነግሯል፡፡ ቢቢሲ እንደዘገበው፤ታዳጊው አሁን በዳይት ላይ የሚገኝ ሲሆን ጥቂት ኪ.ግ ክብደትም ቀንሷል ተብሏል፡፡
በርካታ የኢንዶኔዢያ ህጻናት በከፍተኛ የክብደት መጨመር ችግር እየተሰቃዩ የመሆናቸውን ያህል፣ ብዙዎቹ የአገሪቱ ህጻናት የተመጣጠነ ምግብ እጥረት ተጠቂ እንደሆኑና 8.4 ሚሊዮን ያህል ህጻናት የመቀንጨር ችግር ተጠቂ መሆናቸውን ዩኒሴፍ በቅርቡ ባወጣው ሪፖርት አስታውቋል፡፡

       የአለማቀፉ የገንዘብ ተቋም አይኤምኤፍ ማኔጂንግ ዳይሬክተር ክርስቲያን ላጋርድ፣ እንግሊዝ ከአውሮፓ ህብረት በመውጣቷ ሳቢያ በቀጣዩ አመት ጠቅላላ የአገር ውስጥ ምርቷ ላይ ከ1.5 በመቶ እስከ 4.5 በመቶ ያህል ቅናሽ ሊመዘገብ እንደሚችል አስታወቁ፡፡ ላጋርድ ባለፈው ሰኞ ከለሞንድ ጋዜጣ ጋር ባደረጉት ቃለመጠይቅ፤እንግሊዝ ባለፈው ሳምንት ባደረገቺው ህዝበ ውሳኔ ከህብረቱ አባልነቷ ለመውጣት መወሰኗ ከሌሎች አገራት ጋር በሚኖራት ቀጣይ የንግድ ግንኙነትና በአጠቃላይ ኢኮኖሚዋ ላይ ተጽዕኖ እንደሚኖረው ገልጸዋል፡፡
ውሳኔው አገሪቱ ከተቀሩት የአውሮፓ ህብረት አገራት ጋር ለሚኖራት የንግድ ግንኙነት አሳሳቢ ነው ያሉት ክርስቲያን ላጋርድ፤በእንግሊዝና በአውሮፓ ህብረት መካከል ውሳኔውን በተመለከተ የሚደረጉ ውይይቶች ምን ያህል ጊዜ ሊወስዱ እንደሚችሉ እርግጠኛ አለመሆናቸውን ጠቁመዋል፡፡
የአይኤምኤፍ ዋና ኢኮኖሚስት ሞሪስ ኦብስፊልድ በበኩላቸው፤የቀጣዩ አመት የእንግሊዝና የአለማቀፍ የኢኮኖሚ እድገት ትንበያዎች እንደ አዲስ ይከለሳሉ፤ውጤታቸውም አሉታዊ ይሆናል ሲሉ ባለፈው ሳምንት መናገራቸውም ተዘግቧል፡፡

ተቃዋሚዎቹ ሙጋቤ ስልጣን እንዲለቁ ጠይቀዋል

   የዚምባቡዌ መንግስት ለሰራተኞቹ ደመወዝ መክፈል አልቻለም፤ የአገሪቱን ኢኮኖሚም ወደ ከፋ ቀውስ እየከተተው ነው በሚል የተቀሰቀሰው ተቃውሞ እየተባባሰ መምጣቱንና በመዲናዋ አብዛኞቹ አካባቢዎች የንግድ፣ የትራንስፖርት፣ የጤና፣ የትምህርት አገልግሎት ሙሉ ለሙሉ በሚባል ደረጃ መቋረጡን ሮይተርስ ዘገበ፡፡
የአገሪቱ መንግስት የዶላር እጥረት በማጋጠሙ ከደቡብ አፍሪካ ይገዙ የነበሩ የመሰረታዊ ሸቀጦችን ግዢ መከልከሉን ተከትሎ ባለፈው አርብ ቢትብሪጅ በተባለቺው የአገሪቱ የድንበር ከተማ የሚገኙ ነዋሪዎች ተቃውሞ ማሰማታቸውን የጠቆመው ዘገባው፣ ባለፈው ማክሰኞም በርዕሰ መዲናዋ ሃራሬ የታክሲ አሽከርካሪዎች አደባባይ ወጥተው ተቃውሞ ማሰማታቸውንና ይሄን ተክትሎ ፖሊስ 113 አሽከርካሪዎችንና የተቃውሞው ተሳታፊዎችን ማሰሩ ብዙዎችን ማስቆጣቱንና ተቃውሞውን ማባባሱን ገልጧል፡፡ባለፈው ረቡዕም ደመወዛችን አልተከፈለንም ያሉ የአገሪቱ መምህራንና የጤና ባለሙያዎች የስራ ማቆም አድማ በማድረግ ተቃውሞውን መቀላቀላቸውን የጠቆመው ዘገባው፣ በሃራሬ ሆስፒታሎችና ትምህርት ቤቶች መዘጋታቸውንና በመዲናዋ ከፍተኛ ውጥረት መንገሱን አስረድቷል፡፡አጃንስ ፍራንስ ፕሬስ በበኩሉ፤የሮበርት ሙጋቤ መንግስት ባጋጠመው የኢኮኖሚ ድቀትና የገንዘብ እጥረት ሳቢያ ለመንግስት ሰራተኞች መክፈል የሚገባውን ደመወዝ ከሚገባው ጊዜ ማዘግየቱን በመጥቀስ፣ በመንግስት ላይ ይደረጉ የነበሩ ተደጋጋሚ ተቃውሞዎች ሰሞኑን ተባብሰው መቀጠላቸውንና ፕሬዚዳንት ሙጋቤ ስልጣን እንዲለቁ እስከመጠየቅ መድረሱን ዘግቧል፡፡የአገሪቱ መንግስት የገንዘብ እጥረት በማጋጠሙ ሳቢያ ያልከፈለውን ደመወዝ በስራ መስኮች ከፋፍሎ በቀናት እድሜ ውስጥ ለመክፈል ቃል በመግባት ዜጎቹ ተቃውሞውን አቋርጠው በትዕግስት እንዲጠባበቁ ጥሪ ቢያደርግም፣ ተቃውሞው ከቀን ወደ ቀን እየተባባሰ መቀጠሉን ያመለከተው ዘገባው፤ተቃዋሚዎች ጎዳናዎችን በመዝጋትና ጎማ በማቃጠል ድርጊቶች ላይ መሰማራታቸውንና የአገሪቱ ፖሊስም አስለቃሽ ጭስ መጠቀሙንና በርካቶችን ማሰሩን ገልጧል፡፡


ቻይና በዓለማችን የቴሌስኮፕ ኢንዱስትሪ ታሪክ በትልቅነቱ ቀዳሚውን ስፍራ እንደያዘ
የተነገረለትንና 180 ሚሊዮን ዶላር ወጪ የተደረገበትን እጅግ ግዙፍ ቴሌስኮፕ ግንባታ
ሙሉ ለሙሉ ማጠናቀቋን ሮይተርስ ዘገበ፡፡ ለምድራችን ባዕድ የሆኑ ፍጡራንን በተመለከተ በሚደረጉ ሳይንሳዊ ምርምሮች ላይ መረጃዎችን ለማሰባሰብ ታስቦ በቻይና ብሄራዊ አስትሮኖሚካል ኦብዘርቬሽን ተቋም የተሰራው ይህ ቴሌስኮፕ፣ስፋቱ የ30 የእግር ኳስ ሜዳዎችን ስፋት  ንደሚያክል የተነገረ ሲሆን ግንባታውን ለማጠናቀቅ አምስት አመታት ያህል መፍጀቱ ተዘግቧል፡፡ ይህ ሬዲዮ ቴሌስኮፕ የሬዲዮ ሞገዶችን ከህዋ እያሰባሰበ ወደ አንድ የምርምር ማዕከል የሚያስተላልፍ ሲሆን መጠኑ ትልቅ መሆኑም ከዚህ ቀደም ከተሰሩ ቴሌስኮፖች በበለጠ ሁኔታ፣ እጅግ ያነሱ ሞገዶችን ሳይቀር  መለየት እንደሚያስችለው ተነግሯል፡፡ ከዚህ ቀደም በአለማችን ትልቁ ቴሌስኮፕ የነበረው
በፖርተሪኮ የሚገኘው አርሴቦ ኦብዘርቫቶሪ የተባለ ቴሌስኮፕ እንደነበር ያስታወሰው
የሮይተርስ ዘገባ፣ አዲሱ የቻይና ቴሌስኮፕ ግን ከቀድሞው በአምስት እጥፍ ያህል ግዙፍ
እንደሆነ አስረድቷል፡፡ በደቡብ ምዕራባዊ ቻይና በምትገኘው ጉዚሁ አውራጃ ውስጥ የተተከለው ይህ እጅግ ግዙፍ ቴሌስኮፕ፤በመጪው መስከረም ወር በይፋ ስራ ይጀምራል ተብሎ ይጠበቃል፡፡

(በተለይ ለአዲስ አድማስ )

* የደርግ አባሎችና ርእሰ ብሔር የነበሩ    ፍርዳቸውን ፈጽመዋል  
* መኢሶንና ወዝሊግን ከተከሳሾች መዝገብ    ውስጥ እናስወጣ
* መንግስቱ ኃይለማርያምን ለፍርድ ማቅረብ  ይኖርብናል  
* ኢሕአፓ ደርግን መክሰስ ሙሉ ስራው   አድርጎታል
ለሁለት አስርት ዓመታት ነዋሪነታቸውን በአሜሪካ ያደረጉት የህግ ባለሙያውና ፖለቲከኛው አቶ አሰፋ ጫቦ በቅርቡ ለንባብ ያበቁት ፖለቲካ - ቀመስ መፅሃፋቸው “የትዝታ ፈለግ” ተወዳጅነትን አግኝቶላቸዋል፡፡ አቶ አሰፋ ከአዲስ አድማስ ጋዜጠኛ አለማየሁ አንበሴ በኢ-ሜይል ለቀረበላቸው የተለያዩ ጥያቄዎች ምላሽ ሰጥተዋል፡፡
መፅሐፍ ለማሳተም እስከ ዛሬ ለምን ዘገየህ?
ዘገየህ የሚባል ነገር ያለ አይመስለኝም። በየጋዜጦችና መጽሔቶች በየዘመናቱ የወጣው ተሰባስቦ መጽሐፍ ይሆናል ብዬ አስቤም አላውቅም። ስብስቡም አልነበረኝም። የነበረኝም አንዴ ሎስ አንጀለስ የምኖርባት አፓርትመንት ጣራው ላይ ቧንቧው ፈንድቶ፣ እንደ ጽሕፈት ቤት የምጠቀምበት ክፍል ኮምፒዩተሬንም ጭምር ጨርሶ በላው። የዚህ መጽሐፍ የማድረጉን ሐሳብ ያመነጩት “ያንተን ጽሁፍ እያነበብን ነው ያደግነው!” የሚሉ ወጣቶች ናቸው። አሁን በFacebook ጭምር እንደዚያ የሚሉ ቁጥራቸው ብዙ መሆኑን ተረዳሁ። እንዳለጌታ ከበደና ወሰንሰገድ ገብረኪዳን እዚያው ውስጥ ቅድሚያ ያላቸው ናቸው።
 መቼ፤ ምን ብዬ ጽፌም እንደነበር ያው ከናንተው ጋር ወይም ትንሽ ቀደም ብዬ ነው ያነበብኩት። ሳነበው “እፎይ!” አልኩኝ። “ምነው ባላልኩት!” የምለው ነገር አላገኘሁበትም። ሊጠራ፤ሊሰፋ፤የበለጠ ሊብራራ የሚገባው ሞልቷል፡፡
ቀደም ሲል በተለያዩ የፕሬስ ውጤቶች ላይ ትጽፍ ነበር፡፡ አሁን ግን ከሚዲያ ተሳትፎ እየራቅህ መጥተሃል?
Self-Evident Truth የሚባል አለ። ”የታወቀ ፤የተረጋጋጠ፤ተጨማሪ ማስረጃ አቅርብበት የማይባል!” ለማለት ነው። ለምሳሌ፤አሰፋ ጫቦ ለመሆኔ ማስረጃ ያስፈልጋል። ማስረጃው መታወቂያዬ ነው። ሰፈራችን ውስጥ ሁሉም ሰው ሊያውቀኝ ይችላል። ያ ሌላ የሰፈር፣የመንደር ነገር መሆኑ ነው። አዲስ አበባ የኢትዮጵያ ዋና ከተማ ለመሆኑ ግን ማስረጃ አቅርብ አልባልም። “ምነው?; ቢሉ “አገር ያወቀው ፀሐይ የሞቀው ዕውነት!” ነዋ። “ከሚድያ ተሳትፎ እየራቅህ የመጣኸው ለሚለው ጥያቄ፣ ርቄ ከሆነ ተጠያቂው እኔ ሳልሆን ሜዲያው ነው። ሚዲያው ነው የራቀኝ። ግልጽ ለማድረግ ማራራቅ የሚችሉ ኃይሎች ሚዲያውን ከኔም፤ከሁላችንም አራራቁትና ቦታው ኦና ወይም ወደ ኦናነት ተጠጋ። ጦቢያ፣ኢትኦጵ፣ምንሊክ …ወዘተርፈ የሚባሉት መጽሔቶች፣ መተንፈሻ የነበሩ መድረኮች ተዘጉ። አዘጋጆቹም፤ከርቸሌ ተቀረቀረባቸው። የተረፉትና እድለኞቹ ተሰደዱ። ድረ-ገጹ ሚዲያ ነው ከተባለ ደግሞ ለራሴ ገና ጠርቶ ያልወጡ የውስጥ ማእቀቦች ያሉብኝ ይመስለኛል። የመጀመሪያው፣“ለመሆኑ ስንቱ ኢትዮጵያዊ ነው ከድረገጽ ላይ የሚያነበው?” የሚለው ነው። አብዛኛው፣ ማንበብ የሚችለው ማንበብ ካልቻለ የተመጋቢው ቁጥር በጣም የተመጠነና አብዛኛው የኔቢጤዎች አካባቢ የሚንገዋለል ነው የሚመስለኝ። የሚመስለኝ ማለቴ የተጠና ነገር ስለሌለኝ ነው። ሌላው በአብዛኛው ድረገጽ ላይ፤በተለይም በእንግሊዝኛው የማነበው ብዙም ኢትዮጵያ ኢትዮጵያ አይሸትም የሚለው ፍርሐቴም ሊሆን ይችላል። በኢትዮጵያ ስም የሌሎች አገሮች፤ ህግ፣ ባሕል፤ ስነ-መንግስት፤ታሪክ ሲያመጡ ስለማይ፣ እዚያ ውስጥ የገባሁ እንደሆነ፣ “ውሃ ሲወስድ እያሳሳቀ ነው!” እንደሚባለው እኔንም እዚያ ከቶ ተመሳሳይ ዕጣ ፈንታ እንዳይደርሰኝ  የሚልም ፍርሐት አላጣም። ሌላው፣በሌላ ጊዜ፣በሌላ ቦታ (መድረክ) አንስቼው የነበረ ነው። ሱባዔ ገብቼ ስለነበር ነው። ራስን ፍለጋ (Introspection) ሊባል የሚችል ይመስለኛል። ከዚያ ስመለስ (ስወጣ) ብዙም የተናገርኩ፣ብዙም የጻፍኩ ስለሚመስለኝ ተመልሻለሁ ብዬ አስባለሁ።
በጽሑፎችህ ብዙ ጊዜ ስለ ትውልድ አካባቢህና የተወለድክበት ማህበረሰብ  ዙሪያ ታተኩራለህ የሚሉ አስተያየቶች ይሰነዘራሉ። አንተ ምን ትላለህ?
“የትውልድ አካባቢህ ላይ ታተኩራለህ?” ይህ ብዙ የሚያነጋግር ይመስለኛል። በተለይም በአሁኑ፣“ሁልህም ወደ ክልልህ!” በተባለበት ዘመን። “አንተም ክልልህ ውስጥ ነህ ለካ!” የሚል አንድምታም የሚያጣ አይመስለኝም። ያም ሆነ ይህ እኔ በዚህ ጉዳይ ላይ የትዝታ ፈለግ ላይ ያልኩት አለኝ። “እኔ ጋሞ ነኝ! እኔ ኢትዮጵያዊ ነኝ! እነዚህ ሁለቱ ተጣልተውብኝ ሳስታርቃቸው አልኖርኩም!” የሚል ነው። እኔ እንደማስበው ቁምነገሩ ትውልድ አካባቢ ተተኮረ አልተተኮረ አይመስለኝም። መሆን ያለበት፤ “አተኳኮሩ ጤነኛ ነው ወይ?” የሚለው ይመስለኛል። ጤነኛ ያልሆነ አመለካከት ሕገመንግሥት ደረጃ የደረሰበት ዘመን ውስጥ ነው ያለነውና ከጥያቄው በስተጀርባ ያለው “ጠርጥር!” ይገባኛል። ይህን በዚህ እንዝጋው።
SBS በሚባል ካሳሁን ሶቦቃ በሚያዘጋጀው አውስትራሊያ ባለ ራዲዮ ጣቢያ፤ስለ የትዝታ ፈለግ ስንወያይ፣ “አንተ እንደኔ እንደኔ ሁሉም ኢትዮጵያ እንደ ጋሞ በሆነ ትላለህ!” ብሎኝ፣ ያንን ምን እንዳሰኘኝ አስረድቼ ነበር። SBS ስብስብ (Archive) ስለአለው ቢቻል ያንን ማዳመጡ ጥሩ ይመስለኛል።
ይህ ጥያቄ ሌላም፤ስብሐት ኃይለማርያምንና ማእከላዊንም፤አስታወሰኝ። ስብሐት የባኮ ልጅ ነው። ባኮ ከጅንካ በፊት የገለብና የሐመር ባኮ አውራጃ ይባል የነበረው ዋና ከተማ ነበር። ስብሐት ከብላታ ኃይለማርያም ልጆች ውስጥ አንዱ ነው። ብላታ ኃይለማርያም ደግሞ የመጀመሪያው ወያኔ መስራችና መሪ የነበሩ ናቸው። በዚያ ተከሰው የኃይለ ሥላሴ መንግስት አግዟቸው የኖሩትም፣ልጆቻቸውንም የወለዱትም ባኮ ነው። ደርግ በምህረት ሲለቃቸው፣ አገር አስተዳደር ነበርኩና ብላታ ኃይለማርያን ለአፍታ አነጋግሬአቸው ነበር። ስብሐት የታሰረው በወያኔነት ተጠርጥሮ ነበር። ስብሐት በወያኔነት ታስሮ ግን “የአገሩ ልጅ፤የጋሞ ጎፋ ልጅ!” ብሎ የሚቀርበኝ እኔን ነበር።
አንድ ቀን በረንዳው ላይ ቆመን፣ ያለ የሌለን ስናወራ፣ የጢስ አባይ ፏፏቴ ተነሳ፣ እኔም ጢስ አባይን አውቀው ነበርና፤ሌሎችም ጨምረውበት በማድንቀ፣ስብሐት ቱግ ብሎ፤ “የኛ ይበልጣል! ስላላያችሁት፤ስለማታውቁት ነው እንጅ ባኮ ያለውን ፏፏቴ የሚያስንቅ የትም የለም!” አለ። ”የኛ ይበልጣል!” ነው ያለው። ስብሐት ኃይለማርያም አገሩ፤ተቆርቋሪነቱ ለባኮ፤ብሎም ለጋሞ ጎፋ መሆኑ ነው። ከባኮ፤ከጋሞ ጎፋ ጋር መንፈሱ፣ነፍሱና ስጋው ተዋህደዋል ልንል እንችላለን።
ከስብሐት ሌላ ብዙ ምሳሌዎች ልጠቅስ እችላለሁ። አንድ የሚደንቅ የአማራን ነገር ማንሳት እፈልጋለሁ። በግራኝ ወረራ ጊዜ ታቦታቸውን ይዘው የሸሹ አማሮች ከየትም በላይ ወደ ጋሞ ጎፋ በብዛት የመጡ ይመስለኛል። ለዚህ ማስረጃው የአባ ባህርይ የብርበር ማርያም፤የዶርዜ ጊዮርጊስ፤የኤሌ ገብርኤል አሉ። ጋሞ “ቆሞ” የሚለው ራሱን የሚለይበት መጠሪያ አለው። ክላን (clan) የሚሉትን የእንግሊዝኛው ቃል ይገልጸው እንደሁ እንጃ። ወደ 10 ቆሞ አለ። ከነዚህ 10 ቆሞዎች አንዱ አማራ ነው። አሁን ዶርዜ ሄደው አማራ የት ነው ቢሉ ማንም ያሳያል። የዶርዜ ጊዮርጊስ አጥቢያው ዶርዜ አማራ ነው የሚባለው። የኤሌ ገብርኤል አጥቢያውም ኤሌ አማራ ነው የሚባለው። የጋሞ አማራ የሚለው ቃል አጠራሩ በመሠረቱ እንደሚባለው ሳይሆን ቅላጼው ለየት ይላል። ”ማ’ እና “ራ” ላይ ላላ፤ለቀቅ ይላል። ይህ እንግዲህ ወደ 400 አመት የሚደርስ ታሪክ መሆኑ ነው።
በኔ ግምት ምናልባትም ከየትኛውም አለም በላይ፤በኢትዮጵያም አንጻር ሲታይ፣ ብዙ ብሔረሰብ ያለበት አካባቢ ቢኖር ጋሞ ጎፋ ነው። አሜሪካኖቹ አሜሪካንን Melting Pot ይሉታል። ማቅለጫ ድስት (ሰታቴ) እንደማለት ነው እንበለው። እዚህ የመጣው ህዝብ ሁሉ ቀልጦ አንድ አሜሪካዊ ሆኗል ለማለት ነው። ወረቀት ላይ አንድ ሆኖ እንደሁ እንጅ በድርጊት አሁንም ፈንጠር ፈንጠር ብሎ እንደቆመ ነው። ሰው ቀልጦ ወደ አንድ ሸማ መልበስ የደረሰበት አካባቢ ቢኖር ጋሞ ጎፋ ነው ማለት የምችል ይመስለኛል። “አሻም!” የሚል ሕዝብ ነው። አሻም ከአማርኛው “እንኳን ደህና መጡ!”፤ከእንግሊዝኛው “Welcome” ከፈረንሳይኛም “Beinvenue” ለየት የሚል የማቀፍ ቃና ያለው አቀባበል ነው። ዛሬ በመላው ኢትዮጵያ ባለ- በሌለ፤ከፋብሪካ በወጣ ክስ-ውቅስ ጭምር ያ ሁሉ ንትርክ ሲታይ፣ በአንጻራዊ አነጋገር እጅግ ሰላማዊ አካባቢ ደቡቡ፤በተለይም ጋሞ ጎፋ ነው። ታዲያ ያንን ታሪክ፤ያንን ባህል፣ ይህንን ተመክሮ ለመላው ኢትዮጵያ ለማሳወቅ፤ቢቻልም ለመላው አለም ለማዳረስ የኔ ሙከራ ቅንጭብ (The Tip of the Iceberg) ነች ማለት ነው።
ሌላ ስለ ጋሞ ደጋ የውጭ አጥኝዎችም ብዙ ያሉት አለ። “A Thousand Suns: The View From Ethiopia’s Gamo ...” የሚለውን ፊልም መመልከቱ/ማየት ጋሞ ለስንት ዘመናት፤የመሬት ጥበቃን ስርዐት የያዘ እርሻ ሲያርስ የኖረ ሕዝብ መሆኑን እናያለን። የቋንቋ አጥኝዎች፤የውጭም የኢትዮጵያም የአፍሪቃና የአዚያ ህዝቦች ቋንቋ (Afroasiatic Languages) የሚሉት አለ። ይህ ቋንቋ ቤተሰብ ከሲዳማ እስከ ወለጋ እስከ ባምባሲ የሚዘረጋ ነው። ዝነኛውን የከፋን ንጉሳዊ ግዛትም የሚጨምር ነው። ምናልባትም የዚህ ህዝብ ዋና ቤቱ ጋሞ ሊሆን ይችላል የሚል አዝማሚያ አለ። በቅርቡ ክ4,500 አመት በላይ የሆነ የሰው አፅም ቅሪት ከጋሞ ደጋዎች ተገኝቷል። ”ባይራ!”ብለዉታል። ባይራ ማለት ታላቅ ማለት ነዉ። ይህ ጥንታዊ፣ የሰለጠነና ዘመናዊ የእርሻ ዘይቤ ነበራቸው/አላቸው ከሚባለው ጋር ተደምሮ፣ ጋሞ ጎፋን እንደ ጋና አትኩረን ለማየት የሚጋብዝ ይመስለኛል።
አብዛኛው የናንተ ዘመን ፀሐፊዎች ያለፈ ስርአትን ወቃሽ ናቸው። በየዘመናቱ በነበሩ መንግስታት የተሠሩ በጐ ነገሮችን ለማንሳት ለምን አይሞከርም?
በክስ-በውቅስመልክ መቅረቡ ንጅ ታሪክ የሚባለው’ኮ ያለፈን፣ማብጠልጠል፤ማበራያት፤ፍሬውን ከገለባው፣እውነቱን ከፖለቲካውና ከተረቱ ለይቶ አብጠልጥሎ ማውጣት ይመስለኛል።
 መውቀስ ካልነውም መላ ያለው፤ማስረጃ ያለው ወቀሳም ጥሩ ይመስለኛል። ጅምላ ወቀሳ ከሆነ ደግሞ ወቀሳውንም ወቃሹንም ከፍቶ ማየቱ ጥሩ ይመስለኛል።
ማለትም፣ “ለመሆኑ አንተ ማነህ?”፣ “ከነማን ጋር ነበርክ?”፣ ”ያኔስ የት ነበርክ?”፣ “ምን ምን ሰራህ?”፣ “ምን ምንስ መስራት ሲገባህ ሳትሰራ ቀረህ?”፣ ”በምን ምክንያት?”፣ “ሌላው አይን ውስጥ ያለውን ትቢያ ማሳየት ብቻ ሳይሆን አንተስ አይን ውስጥ የተጋደመውን ግንድ ምን እናደርገው?” ማለቱ ጥሩ ይመስለኛል።
“የእናንተ ዘመን ጸሐፊዎች” ሲባል እኔ እንደሚገባኝ ይህንን፤በ1950ዎቹ አጋማሽ ጀምሮ ያለውን፤የኢትዮጵያ ተማሪዎች ንቅናቄ ተብሎ የሚታወቀውን፤በአሜሪካና በአውሮጳም ቅርንጫፎች የነበሩትን፤ዘውዱ ወርዶ ከደርግም ጋር ጎራ ለይተው የተፋለሙትንና የተላለቁትን፣አሁንም በርዝራዥ መልክም ቢሆን መንግስት የሆኑትና ተገፍተው ወጥተው ዳር ቆመው “እኔ/ እኛ አይደለንም፤ እነሱ ናቸው!” የሚለውን የምናስተጋባውን ይመስለኛል።
ተከሳሹ ሁሌም ደርግ ነው። ሻዕቢያ፤በወያኔ አማካኝነት “ኤርትራ የኢትዮጵያ ቅኝ ግዛት ነበረችና አሁን ነጻ ብትወጣ እደግፋለሁ!” የሚል ደብዳቤ ለተባበሩት መንግስታት ድርጅት ጽፈው ነጻ ወጥተዋል። ስለዚህ ሻዕቢያ ዛሬ፣በአሁን የክሱ ችሎት ውስጥ የለም። የቀሩት ከሳሾች በጋራም ሆነ በተናጠል የሚከሱት ደርግን ነው።
ይህንን የደርግን ተከሳሽነት በሕግ አንጻር እንየው። አንድ ተከሳሽ ፍርድ ቤት ቀርቦ፤ ጉዳዩ ተሰምቶ፣ ፍርድ ከተሰጠበትና በፍርዱ መሠረት ቅጣቱን ተቀብሎ ከፈጸመ የድርጊቱን ከፍሏል ማለት ነው። የደርግ አባሎችና ርእሰ ብሔር የነበሩ ብቻ ሳይሆን ከደርግ ጋር ነበሩ የሚባሉ፤በወያኔ ቋንቋ ንክኪ የሆኑ ሁሉ ታስረው፣ ማቀው፣ ፍርዳቸውን ፈጽመው ተለቀዋል። መሪዎቹ የሚባሉት የተለቀቁት ከ20 አመት በኋላ ነበር። ብዙዎቹ ከርቸሌ ነበር የሞቱት። ይህም ማለት በክስ መልክ የደርግ ፋይል እስከ ወዲያኛው ተዘግቷል ማለት ነው። ደርግን አሁን መክሰስ፣ እዚህ እኔ ያለሁበት አገር Double Jeopordy ይሉታል። ለዚያው ወንጀል ሁለቴ መክሰስ እንደ ማለት ነዉ። ሕግ አይፈቅድም! ከአሁን በኋላ የደርግ ነገርና ዘመን የሚያገለግለን ለሰከነ የታሪክ ጥናትና ምርምር ብቻ ነው። የደርግ ከሳሾች፤ ይህንን ልብ ሊሉ ይገባል፡፡ ”እስከ ሰባት ትውልድ እበቀልሀለሁ!” ኦሪት ነው። ሐዲስ ተክቶታል! ይልቁንም ለዚህ ሁሉ ክስና- ውቅስ በአብዛኛው የዳረገንን ፤መንግስቱ ኃይለማርያምን እንዴት አድርገን ፍርድ አደባባይ እናድርስ የሚለውን ብንመክርበት የተሻለ ይመስለኛል።
መኢሶንና ወዝሊግን ከተከሳሾች መዝገብ ውስጥ ማስወጣት ያለብን ይመስለኛል። ቀይ ሽብር ነጭ ሽብር ተብሎ የኢትዮጵያን ቀጣይ ትውልድ በፈጀውና የደርግ አባላትንም እርስ በርስ በማባላት የተጫወቱትን ሚና ሌሎች የጻፉት እንደተጠበቀ ሆኖ፤ ፍቅረ ሥላሴ ወግደረስና ፍስሀ ደስታ ደህና አድርገው ገልጠዉታል። ያም ሆኖ፣ መኢሶኖች በተለየ አይቀጡ ቅጣት ተቀጥተዋል። መንግስቱ ኃይለ ማርያም፤የመኢሶንን መሪዎች አርዷቸዋል። ከዚህ በላይ የሚከፈል ዋጋ ሊኖር ስለማይችል፣ ከደርግ ጋር በማበር የፈጸሙትን ወንጀል መዝገብ ዘግተን፣ ወደ መዝገብ ቤት በቋሚነት መመለስ ያለብን ይመስለኛል። አሁን ያለው ትንሹ ችግር በሕይወት የተረፉት ይህንን የክስ መዝገብ ያልዘጉ መሆናቸው ነው። ስለ ኢትዮጵያ ፖለቲካ ለምን ተናገሩ? ለምንስ ይናገራሉ? አይደለም። ንስሀ መግባት ግን አማራጭ ያለው አይመስለኝም።
አሁን የሚቀሩን ሁለት ፤ሙሉ ሥራቸውና ከፊል ሥራቸው ወቃሽ የሆኑ ናቸው። እነሱም ኢሕአፓና ወያኔ ናቸው። ኢሕአፓ ደርግን መክሰስ ሙሉ ስራው ማድረጉ ብቻ ሳይሆን አዲስ፣ ደርግንም ኢሕአፓንም የማያውቁትን አሰልጥኖ፣ በከሳሽነትና-ወቃሽነት አሰማርቷል። እዚህ አሜሪካ፤ “እገሌ በደርግ ጊዜ ቀበሌም….እዚህም… እዚያም ነበር” እንዲሉ ስራ የተሰጣቸው እድሜያቸው 30ው ውስጥ የሆኑ አሉ። ለመጭው ትውልድ ውርስ መሆኑ ነው። ስለ ደርግ መጥፎነት፤ስለ ኢሕአፓ መስዋእትነት እንጅ የነገሯቸው ሙሉ እውነት የለም። ቢያንስ ከነዚህ አንዱን “ለመሆኑ ስለ ኢሕአፓ ምን ምን ታውቃለህ?” ብዬው ነበር። “ለኢትዮጵያ የቆመ ብቸኛው ድርጅት; መሆኑን ብቻ እንጅ ሌላ ምንም የሚያውቀው አልነበረም። “ጌታቸው ማሩን ታውቀዋለህ?” አያውቀውም።
ያ እንዳለ ይሁን እንበል። ከሁሉም በላይ ግን የኢሕአፓ ሙሉ ለሙሉ ያልተወራረደ ሂሳብም አለ’ኮ። በዚያ ይባስ ብሎ ደግሞ ሂሳቡን ሊያወራርዱ የሚችሉ ከመሪዎች ውስጥ የተረፉ፣ በሕይወት ያሉት ሁለቱ፤ክፍሉ ታደሰና እያሱ አለማየሁ ብቻ ይመስሉኛል። እንደምገምተው፤ሁለቱም እድሜያቸው እንደኔው 70ው ውስጥ ይመስለኛል። “ለንስሀ ሞት አብቃኝ!” የሚባልበት እድሜ መሆኑ ነው።
እንደሚታወቀው የኢሕአፓ አስኳሉ የአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ ተማሪዎች ማህበር (አአዩተማ) ነበር። እኔም እዚያው ነበርኩ። ማሕበሩ የተሰባሰበው በሁለት ሰንደቆች ዙሪያ ነበር። እነዚህም ፡-1. የዘውድ አገዛዝ ይብቃው (ይውደም) 2. መሬት ላራሹ ነበሩ።
መስከረም 2,1967 የዘውድ አገዛዝ በኢትዮጵያ ለአንዴም ለዘለዓለምም አከተመ። የካቲቲ 25,1967 የገጠር መሬት አዋጅ ታውጆ፣ መሬት ላራሹ ሆነ። የአአዩማ ጥያቄ መልስ አገኘ ማለት ነው። የቀረ የሚሟላ የለም ማለት አይደለም። የትግላችን እምብርት ጥያቄ የነበረው መልስ አግኝቷል ማለት ነው።እስቲ አሁን ደግሞ ኢሕአፓ ያደረጋቸውን፤በግልጽ በራሳቸው በተለይም በመሪዎች በክፍሉ ታደሰና በብርሐነ መስቀል ረዳ ከተነገሩን ብቻ ልጥቀስ።በኋላ የኢሕአፓ መሪ የሆኑት ብርሐነ መሰቀል ረዳና እያሱ አለማየሁ፤ ፈር ቀዳጅ ሁነው የኢትዮጵያ አየር መንገድ አውሮፕላን ጠላፊዎች ነበሩ። ከዚያ በኋላ ሌላ 4 ጊዜ ተጠለፈ። አምስቱንም ጠላፊዎች ያቀነባበረው ጀበሀና ሻአቢያ ነበረ። ይህንን የሚነግረን ክፍሉ ታደሰ “ያ ትውልድ” በሚለው መጽሐፉነው።
ኢሕአፓ ትግራይ ውስጥ፣ አሲምባ የሚባል ቦታ ምሽግ የከፈቱት የካቲት 25 ቀን 1967 ነበር። ይህንን የሚነግረን ብርሐነ መስቀል ነው። መሬት ላራሹ ያሉት፣ መሬት ላራሹን ያወጀን መንግስት ለመውጋት ጫካ የገቡበትን ቀን ልብ ይሏል። (መሬት ለአራሹ) የታወጀ ለት ነበር!) ለሁለት አመት ያክል አስልጥኖ፤መሳሪያ አስታጥቆ፤ስንቅ ሰንቆ አሲምባ ያስገባቸው ሻቢያ ነበር።
ክፍሉ እንደሚነግረን፤ ሶማሌያ ከሲአድ ባሬም ጋር ነበሩ። ሶማሌ ኢትዮጵያን ስትወር፣ የኢትዮጵያን ወታደር ከውስጥ በ5ኛ ረድፈኝነት ወግተዋል። የገጠር መሬት አዋጅን ስራ ላይ ለመተርጎም የዘመተውን በትነዋል። በመላው ኢትዮጵያ ከተማ ከሕጻን እስከ አካለ ስንኩል (የምኒልክ ትምህርት ቤት ዲሬክተር) በየመንገዱና በየቢሮው ገድለው ጥለዋል። የመድኃኔአለም ትምህርት ቤት ተማሪ ሰቅለዋል። ቀበና ወንዝ ውስጥ ፈጥፍጠው ገድለዋል። ጌታቸው ማሩን መግደል ብቻ ሳይሆን በአሲድም አቃጥለዋል። ጫካ ለውጊያ ያሰማሯቸውን፤ይርጋ ተሰማን ጨምሮ በመቶ የሚቆጠሩ፣መጀመሪያ እስኪቀምሉ ጉድጓድ ውስጥ አስረው አማቀው፣በመጨረሻም ረሽነዋቸዋል። የገደሉትን ሰው ቁጥር በከፊልም ቢሆን ፍቅረ ሥላሴ ወግደረስ በመጽሐፉ ገልጾታል። ኢሕአፓ ከሻቢያም ብቻ ሳይሆን የወያኔ ተባባሪ፣ዛሬም የኢህዴግ አባል ነው። የመጀመሪያው የኢህአዴግ ጠቅላይ ሚንስቴር ፤ታምራት ላይኔ፤ምክትል ጠቅላይ ሚንስትሩ አዲሱ ለገሰ ኢሕአፓ የነበሩ ናቸው። አሁን ብአዴን ሆነናል የሚሉት አክሮባቲክስ አንደተጠበቀ ሆኖ።ይህ ያልተዘጋ ቁስል ነው። መልስ የሚፈልግ ነው። ኢሕአፓ ደርግም ላይ ሆነ ወያኔ ላይ ጣቱን ከመቀሰሩ በፊት ለዚህ ክፍት ለተቀመጠ ቁስላችን መዝጊያ መስጠት ያለበት ይመስለኛል። (እናም ኢሕአፓ ውስጥ ያለችው “ኢ” ኢትዮጵያ መሆንዋ ነው።) በዚህ ድርጊታቸው ውስጥ ለመሆኑ ኢትዮጵያ አለችበት የሚለውም ጥያቄ መልስ የሚሻ ይመስለኛል።የወያኔ ጉዳይ በመሠረቱ ህግ ውስጥ Mutatis mutandis የሚሉትን አይነት ይመስለኛል። በግዕዙ ዚኒ ከማሁ የሚባለው ነው። አነሰም በዛ ከላይ እንደተገለጸው እንደ ማለት ነው። ይህም ማለት ቀደም ሲል ስለ ኢሕአፓ ያልኩት ለወያኔም ያገልግላል። ለምሳሌ፣ ወያኔ የተነሳው፣የተመሠረተው ከደርግ መጥፎ አገዛዝ ነጻ ለመውጣት አይደለም። ደርግ አልነበረምና አይተዋወቁምና ነው። ደርግ ንጉሱን በማውረዱ በተፈጠረው ክፍተት ትግራይን ነጻ ለማውጣትና የትግርይን ሬፑብሊክ ለመመስረት ነው። የመጀመሪያው የእነብላታ ኃይለ ማርያም ቀጣይ መሆኑ ነው። ይህ ሰነዳቸው የሚመስከረው ነው።
ንፁህ ህዝብም ሆነ ወይም ተቃዋሚ ነው ተብሎ የተፈረጀ በመፍጀት ከኢሕአፓ ቢበልጡ እንጅ አይተናነሱም። ልዩነቱ (እስከ 1983 ግንቦት መሆኑ ነው) የወያኔ አባሎቻቸው በነበሩትም ሆነ በሕዝብ ላይ የተፈጸመው ግፍ ከኢሕአፓ የሚለየው ትግራይ ውስጥ ብቻ በመሆኑ ነበር። ----- አንድ ነገር ልብ ብንል የሚሻል ይመስለኛል። ባለፈው ወር የተባበሩት መንግስታት የሰብአዊ መብት ኮሚሽን፣ በኤርትራ ጉዳይ ያቋቋመው ቡድን፣ስለ ኤርትራ መንግስት የሰጠውን ሰፊ ሪፖርት ልብ ይሏል። ያ ሠነድ ሲታይ፣ስለ ኢትዮጵያ ጭምር ይሆን? የኢትዮጵያ መንግስትን ከዚያ ውስጥ የሚመለከተው ክፍል ስንት እጁ (%) ነው? የሚል ጥያቄ መነሳት ያለበት ይመስለኛል፡፡

    ከዕለታት አንድ ቀን አንዲት አሮጊት ከእንቅልፋቸው ሲነቁ የማይታመን ነገር አዩ፡፡ ግቢያቸው በጎርፍ ተጥለቅልቋል፡፡ ውሃው የምድር ቤቱን አጥለቅልቆ ጨርሶ የመጀመሪያውን ፎቅ ሞልቶታል፡፡ አሰቃቂው ነገር ደግሞ ከደቂቃ ደቂቃ፣ ከሰዓት ሰዓት ገና ማጥለቅለቁን እየቀጠለ፣ እያደገ ነው፡፡
አሮጊቷ ከመኝታ ቤታቸው ወደ ውጪ ሲያስተውሉ፣ ጎርፉ ገና ካፋፍ ወደ ታች እየተንደረደረ ነው፡፡ ከፍታውም አፍታ በአፍታ እያደገ ነው፡፡ ሁለት ሰዎች በእጅ በምትቀዘፍ ጀልባ ሆነው በአሮጊቷ ቤት አጠገብ ሲያልፉ፤
“እማማ፣ እማማ፣ ኧረ እማማ!” ብለው ጮኸው ይጣራሉ!
“እመት፤ ምን ፈልጋችሁ ነው?”
“ይውረዱ፡፡ አብረን እንድናለን፡፡ እባክዎ ይምጡ!” አበክረው አሮጊቷን ለመኗቸው፡፡
“አመሰግናለሁ ሂዱ” አሉ አሮጊቷ፡፡ “ለእኔ እሱ የላይኛው ያውቅልኛል” ብለው ወደ ሰማይ አመለከቱ፡፡ አምላካቸው እንደሚያድናቸው በመተማመን መናገራቸው ነው፡፡
ባለ ጀልባዎቹ ትከሻቸውን ከፍ ዝቅ አድርገው፤ እኛ ምንቸገረን በሚል ስሜት በጀልባቸው እየቀዘፉ መንገዳቸውን ቀጠሉ፡፡ ማታ ገደማ ውሃው አድጎ አድጎ የመኝታ ክፍላቸውን ወደ ማጥለቅለቅ እየመጣ በመሄዱ፤ አሮጊቷ ያላቸው አማራጭ ጣራው ላይ መውጣት ሆነ፡፡ አሮጊቷ ጣራው ላይ ወጡ፡፡ አንድ ባለሞተር ጀልባ እንዳጋጣሚ ብቅ አለና አያቸው፡፡ ከዚያም፤
“እማማ” ሲል ጮኾ ተጣራ፡፡
“አቤት የእኔ ልጅ” አሉ የሞት ሞታቸውን፡፡
“አይጨነቁ፤ መጥቼ አወርድዎትና በሞተር ጀልባ እንሄዳለን!”
አሮጊቷም፤
“ግዴለህም ልጄ በምንም አትቸገር! ለእኔ እሱ የላይኛው ያውቅልኛል፡፡ አንተ ሂድ በሰላም ግባ” ይሉታል፡፡ ጀርባቸውን ያዞሩበታል፡፡ ሞተሩን ቀስቅሶ እሱም መጭ ይላል!
አሮጊቷ ምንም ሳይቆዩ ጎርፍ ጣራውን ማጥለቅለቅ ስለጀመረ፤ ከጣራው በላይ ወዳለው ወደ ብቸኛው፣ እስካሁን ጎርፍ ወዳልነካው፣ ቦታ፤ ወደ ጭስ ማውጫው አናት ወጡ! እንደ ዕድል ሆኖ የቀይ መስቀል ጎርፍ መከላከያ ቡድን ወደ አሮጊቷ ቤት አጠገብ ይመጣል፡፡
“ወደ ትልቁ ጀልባ ይዝለሉ እማማ!” አለ ከመከላከያ ቡድን አባላት አንዱ፡፡
አሮጊቷ ራሳቸውን ነቀነቁና ኮስተር ብለው፤
“እሱ የላይኛው ያውቃል፡፡ እሱ የትም አይጥለኝም!” ይላሉ፡፡ ትልቁ ጀልባም፤ እየተምዘገዘገ የአሮጊቷን ቤት አልፎ ሄደ፡፡ ውሃው ማደጉን አላቋረጠም፡፡ እስከ ጭስ ማውጫው አናት ደረሰና አሮጊቷን ዋጣቸው፡፡ አሮጊቷ ውሃው እየዋጣቸው ሳሉ ፀሎታቸውን ለአምላካቸው አሰሙ፡፡
“ምነው አምላኬ! አንተን አምኜ ጉድ ታረገኝ?” ሲሉ አማረሩ፡፡
አምላክም እንዲህ ሲል መለሰላቸው፤
“አንቺ ሴት! ችግርሽን አይቼ ሶስት ጀልባ ላክሁልሽ፡፡ ያውም በመጀመሪያ በእጅ የሚዘቀፍ ትንሽ ጀልባ፡፡ ምናልባት ጥሩ ኑሮ ትኖሪ ስለነበር ትንሹን ጀልባ አልቀበልም ያልሺው ያንሰኛል ብለሽ ይሆናል ብዬ! ቀጥዬ በሞተር የሚነዳ መካከለኛ ጀልባ ላኩልሽ፡፡ እሱንም አሻፈረኝ አልሽ፡፡ በሶስተኛው ትልቁን ጀልባ፣ ከነትልቅ ሞተሩ፤ ሊያውም ከነሰራተኞቹ ላኩልሽ፡፡ በጭራሽ አልቀበልም አልሽ! ከዚህ በላይ ምን ላድርግሽ?! ከእንግዲህ የራስሽን መንገድ ፈልጊ!” አላቸው፡፡
*       *       *
ጎርፉንም ድርቅንም ካልተቆጣጠሩት ለከፍተኛ አደጋ እንደሚያጋልጥ እንገንዘብ፡፡ ሲረዷቸው የማይረዱ አያሌ ናቸው፡፡ በዓመታትና በወራት ጊዜ ውስጥ ሳይሆን በቀን ውስጥ ከተከሰተው የማይማሩ ብዙ ናቸው፡፡ ጎርፍ መምጣቱን፣ ክረምት መግባቱን እዩ፤ አጥራቸውን ማጠርን፣ እርከናቸውን መስራትን፣ ጣራቸውን ማጠንከርን የማይሹ በርካታ ናቸው፡፡ ኑሮ መቼም ሞልቶ አያውቅም፡፡ ውጣ ውረድ አለው፡፡ በሁሉም መልክ ጥረትና ትግልን ይጠይቃል፡፡ የአንዳንዱ ኑሮ ውሃ ወቀጣ ነው፡፡ የአንዳንዱ የዘነጋ ተወጋ ነው፡፡ የአንዳንዱ ከድጡ ወደ ማጡ ነው፡፡ አንዳንዱ ወፍራም ውሻ፣ አለ ሲሉት ይሞታል ነው፡፡ ወረቀት ላይ ያስቀመጥነው ዕድገት የሰውየውን መሶብ እንዴት አድርጎት ይሆን ብሎ መጠየቅ ተገቢ ነው፡፡ አለበለዚያ ድህነት ላይ የምናሰግረው መፈክር የወረቀት ላይ ነበር (Paper tiger እንዲሉ) ያደርገናል፡፡
ነጋ ጠባ የሚወራለት የመልካም አስተዳደር ችግር ዛሬ ቁስሉ ዳነ ሲባል፣ ነገ እያመረቀዘ የቆላ ቁስል ይሆንብናል፡፡ ጨርሶ ወደ ማይድን በሽታ፣ ወደ ጋንግሪንነት፤ እንዳይሄድ መጠንቀቅ ተገቢ ነው፡፡ የከፋው ችግር ደግሞ ለሙስናውም፣ ለዲሞክራሲዓዊና ለመብት ጥያቄውም፣ ለፍትሕ መጓደልም ወዘተ “ተጠያቂው መልካም አስተዳደር ነው” ማለቱ ሲሆን ዕውነቱን ከማደብዘዝም አልፎ ፈር ያስተዋል፡፡ የሀገራችን ሌላው ቁልፍ ችግር፣ ቤተ-ሰሪ ለፍቶ ለፍቶ “ደም - የለውም” እስኪባል ድረስ ቅርሱን ጨርሶ፣ ቤት ሰርቶ “ፊኒሺንጉ” ያስቸግራል እንደሚባለው፤ በጣም ያስቸግራል ይላሉ፡፡ ይሄንን በቀላሉ ለመረዳት የኳስ ቡድናችንን ማጤን ነው፡፡ ሁሌ እግብ ጋ ሲደርሱ አይሳካላቸውም እንደሚባለው ነው - “የአፈፃፀም ችግር” አለባቸው የተለመደች አባባል ናት፡፡ ስንት ዘመን የዚህ ችግር ቁራኛ እንሆናለን? ነው ወይስ እየደጋገምነው አዋቂው እንዳለው፤ “ትለምጂዋለሽ” ሆኖ አረፈው፡፡ የበጀት መዝጊያ ሲደርስ “ምንጣፍ መግዛት” የአፈፃፀም ችግርን መቅረፍ ነውን? ወይስ በዘመኑ ቋንቋ “የአፈፃፀም ችግር “ውስጤ ነው” በሚል “ቃና” የምናልፈው ጣጣ ይሆን? የችግሮቻችን ብዛትና የመፍትሔ አሰጣጣችን አቅም ሲታይ፣
“በነጠላ ጫማ፣ ባንቺ አረማመድ
እንዴት ያልቅልሻል ያ ሁሉ መንገድ!” የሚባለው ህዝባዊ ዘፈን ግጥም ዓይነት ነው፡፡ ስለዚህ ጉዳይ ብዙ የወተወትነው በሥራ እንለወጥ ዘንድ እንጂ እንደው የማንጓጠጥ ወግ ለማምጠቅ አይደለም፤ በቀና መንፈስ ነው፡፡
“ለትምክህት አይደለም፣ ይህን መናገሬ
ለማስቀናት እንጂ ሰነፉን ገበሬ፡፡
ሃዋርያው ሲናገር ወደ ምዕመናኑ
ለምትበልጥ ፀጋ ይላል ቅኑ አስቀኑ!”
እንዳለው ነው፡፡
በህዝብ ተዓማኒነትን ለማፍራት የመሞከር ጉዳይ በመንግስት ልዩ ትኩረት ሊሰጠው የሚገባ ነገር ነው፡፡ በኦሮሚያ ግጭት ነበር፡፡ በአማራ ክልል ግጭት ነበር፡፡ በአዲስ አበባም ግጭት ነበር፡፡ በወለጋም ግጭት ነበር፡፡ ግጭትን በእልህ ሳይሆን በዘዴ፣ በብልህነት ለመፍታት መሞከር፣ ካለፈው ትምሀርት መውሰድ፣ ዋና መንገድ ነው፡፡ ሌላው ቁልፍ መንገድ ከጎረቤቶቻችን ጋር ያለን ዲፕሎማሲያዊ አካሄድ ነው፡፡ አንዱን በዱላ አንዱን በመላ፤ የሚለው አያያዝ መፈተሽ አለበት፡፡ ዲፕሎማሲያችን፤ “የሀፍረተ-ስጋህን ፀጉር የምታሳየው አለ፡፡ የብብትህን ፀጉር የምትከለክለው አለ፡፡” የሚለውን ልብ ይበል፡፡

   ጅማ ዩኒቨርሲቲ ከኤቢኤች ሰርቪስ ጋር በመተባበር በሁለት የድህረ ምረቃ ፕሮግራሞች ያስተማራቸውን 136 ተማሪዎች ነገ በሸራተን አዲስ ያስመርቃል፡፡
በማስተርስ ኦፍ ቢዝነስ አድሚኒስትሬሽንና በማስተርስ ኦፍ ፐብሊክ ኸልዝ የሚመረቁት እነዚሁ የድህረ ምርቃ ተማሪዎች፤ ላለፉት ሁለት ዓመታት በአዲስ አበባ ኤቢኤች ካምፓስ ትምህርታቸውን ሲከታተሉ የቆዩ ናቸው፡፡
ዩኒቨርሲቲው የረጅም ዓመታት ሙያዊ እውቀትና ልምድ ያላቸውን መምህራን በመመደብ ተማሪዎቹን በማስተማር ላይ እንደሚገኝ የገለፁት የዩኒቨርሲቲው ፕሬዚዳንት ፕሮፌሰር ፍቅሬ ለሜሳ፤ አሁንም አዳዲስ ፕሮግራሞችን በመክፈት የመንግስትና የግል ዘርፉን አጋርነት ወደ ላቀ ደረጃ ለማድረስ እንደሚሰራ ገልፀዋል፡፡
 የኤቢኤች ሰርቪስ ዋና ሥራ አስፈፃሚ ዶ/ር ማርቆስ ፈለቀ በበኩላቸው፤ የጅማ ዩኒቨርሲቲን ወደ አዲስ አበባ መምጣት ተከትሎ የድህረ ምረቃ ተማሪዎች ፍላጎት ከጊዜ ወደ ጊዜ እየጨመረ መሄዱን ጠቁመው፤ በቀጣዩ በሁለት የድህረ ምርቃ ፕሮግራሞ በፐብሊክ ሪሌሽንና ኮርፖሬት ኮሚዩኒኬሽን እንዲሁም በኸልዝ ሞኒተሪንግና ኢቫሉዬሽን አዳዲስ ተማሪዎን እንደሚቀበል ተናግረዋል፡፡
ዩኒቨርሲቲው በነገው ዕለት ከሚያስመርቃቸው የድህረ ምረቃ ተማሪዎች መካከል 42ቱ ሴቶች ሲሆኑ ባለፈው ዓመት ለመጀመሪያ ጊዜ 97 ተማሪዎችን በሁለተኛ ዲግሪ አስተምሮ ማስመረቁ አይዘነጋም፡፡ 

የከተማዋ ስራ አጦች ሁለት ወጣቶች ብቻ ናቸው

   ኬታንጋታ የተባለቺውና 800 ነዋሪዎች ብቻ ያሏት የኒውዚላንድ ከተማ “እጅግ ብዙ ክፍት የስራ ቦታና አነስተኛ ዋጋ ያላቸው የመኖሪያ ቤቶች ቢኖሩኝም፣ ይህን ዕድል የሚጠቀምበት ሰው አጥቼ ተቸግሬያለሁ፣ እባካችሁ ኑ ወደ እኔ” ማለቷን ቢቢሲ ዘገበ፡፡ የሰው ሃይል እጥረት ያጋጠመው የከተማዋ አስተዳደር ችግሩን ለመቅረፍ፣ የሌሎች የኒውዚላንድ ከተሞች ነዋሪዎችን እባካችሁ ኑልን ሲል ጥሪ ያሰተላለፈ ሲሆን፣ የከተማዋ የስራ አጦች ቁጥር 2 ብቻ ነው ሲሉ ከንቲባው ማስታወቃቸውንም ገልጧል፡፡ ከንቲባው ወደ ከተማዋ ለሚመጡ አዳዲስ ነዋሪዎች፣ የመኖሪያ ቤት በእጅግ አነስተኛ ዋጋ ከማቅረብ ባለፈ፣ሌሎች በርካታ ማበረታቻዎችን ለማድረግ ማቀዳቸውንም አስታውቀዋል፡፡ በከተማዋ ካሉ ክፍት የስራ ቦታዎች መካከል የመነሻ ደመወዛቸው እስከ 26ሺህ 500 ፓውንድ የሚደርሱ እንደሚገኙበት የጠቆመው ዘገባው፤ አስተዳደሩ በህክምና፣ በህንጻ ግንባታ፣ በወታደራዊ ሃይልና በሌሎች በርካታ ዘርፎች ያሉትን ክፍት የስራ ቦታዎች ዝርዝር ይፋ ማድረጉንም ገልጧል፡፡

ኢትዮጵያ ከ178 የዓለም አገራት ባለመረጋጋት 24ኛ ደረጃን ይዛለች

የዓለማችንን አገራት ያለመረጋጋት አደጋ ደረጃ በየአመቱ ይፋ የሚያደርገውና ፈንድ ፎር ፒስ የተባለው ተቀማጭነቱ በአሜሪካ የሆነው የምርምር ተቋም ባለፈው ረቡዕ ባወጣው የ2016 አመታዊ ሪፖርት፤ ሶማሊያ ከፍተኛ ያለመረጋጋት ችግር የታየባት ቀዳሚዋ የአለማችን አገር መሆኗን አስታውቋል፡፡
የአገራትን አጠቃላይ ሁኔታ የሚያመለክቱ በሺዎች የሚቆጠሩ ሪፖርቶችንና ጽሁፎችን በመተንተን እንዲሁም ማህበራዊ፣ ፖለቲካዊና ኢኮኖሚያዊ ሁኔታዎችን የሚያመላክቱ 10 ቁልፍ መስፈርቶችን መሰረት በማድረግ ደረጃ የሚሰጠው ተቋሙ፤ ለ12ኛ ጊዜ ባወጣውና 178 የአለማችን አገራትን ባካተተው ሪፖርቱ፣ ሶማሊያን በቀዳሚነት አስቀምጧታል፡፡ከሶማሊያ በመቀጠል ከፍተኛ ያለመረጋጋት ችግር ያለባት አገር ደቡብ ሱዳን እንደሆነች የጠቆመው ሪፖርቱ፤ መካከለኛው አፍሪካ ሪፐብሊክ፣ ሱዳን፣ የመን፣ ሶርያ፣ ቻድ፣ ዲሞክራቲክ ሪፐብሊክ ኮንጎ፣ አፍጋኒስታንና ሃይቲ እስከ አስረኛ ያለውን ደረጃ እንደያዙ ገልጧል፡፡ኢትዮጵያን በ24ኛ ደረጃ ላይ ያስቀመጠው የዘንድሮው ፈንድ ፎር ፒስ ሪፖርት፤ አገሪቱ ባለፉት አራት አመታት የመረጋጋት ሁኔታዋ እየተሻሻለ  ቢመጣም፣ በአገሪቱ የቡድን ግጭቶችና የተማረ የሰው ሃይል ፍልሰት ከአምናው ጋር ሲነጻጸር ጭማሪ አሳይቷል ብሏል፡፡
ከአለማችን አገራት መካከል እጅግ ዘላቂ የሆነ መረጋጋት ያለባት አገር ፊንላንድ ናት ብሏል የተቋሙ ሪፖርት፡፡