Administrator

Administrator

- ቡድኑ 5 ኢትዮጵያውያን አባላት አሉት ተብሏል
- በስደተኞች ጀልባ አደጋ ከሞቱት መካከል አንደኛው ኢትዮጵያዊ ነው ተባለ

   በኩዌት በቤት ሰራተኝነት ተቀጥረው የሚሰሩ ኢትዮጵያውያን ሴቶችን ከቀጣሪዎቻቸው ቤት በማስኮብለል ህጋዊ ባልሆነ መንገድ ሌላ ቦታ በማስቀጠርና ገንዘብ በመሰብሰብ ህገወጥ ስራ ላይ ተሰማርቷል የተባለ ቡድን ከትናንት በስቲያ በፖሊስ ቁጥጥር ስር መዋሉን ገልፍ ዲጂታል ኒውስ ድረገጽ ዘገበ፡፡
አምስት ኢትዮጵያውያንን በአባልነት የያዘውና ህጋዊ ፍቃድ ሳያወጣ በተጭበረበረ ሰነድ የሚንቀሳቀሰው ይህ ቡድን፣ በአገሪቱ የሚገኙ ኢትዮጵያውያን የቤት ሰራተኞችን ከፍ ባለ ደመወዝ እናስቀጥራችኋለን እያለ ከተቀጠሩበት ቤት በማስኮብለል በድብቅ ቦታ እያቆዩ ለሌሎች ቀጣሪዎች ይሸጣል መባሉን ዘገባው ገልጧል፡፡
ከቡድኑ ጋር ይሰራሉ የተባሉ ኢትዮጵያውያንና የሌሎች የአፍሪካ አገራት ዜግነት ያላቸው 17 ወንዶችና 13 ሴቶችም በፖሊስ ቁጥጥር ስር ውለዋል ያለው ዘገባው፣ የቡድኑ አባላትና ተባባሪዎቻቸው ለፍርድ ቀርበው ህጋዊ እርምጃ እንደሚወሰድባቸው አስታውቋል፡፡በተያያዘ ዜና የተለያዩ የአፍሪካ አገራት ስደተኞችን ጭና በሜዲትራኒያን ባህር ላይ ስትቀዝፍ በነበረች ጀልባ ላይ ከትናንት በስቲያ በደረሰ የመስጠም አደጋ ለህልፈተ ህይወት ከተዳረጉትና አስከሬናቸው ከተገኘ 9 ሰዎች መካከል አንደኛው ኢትዮጵያዊ እንደሆነ መረጋገጡ ተዘግቧል፡፡
የግብጹ ዴይሊ ኒውስ ድረገጽ ያወጣው ዘገባ፣ በአደጋው ለህልፈተ ህይወት የተዳረገው ኢትዮጵያዊ የ43 አመት ጎልማሳ መሆኑ መረጋገጡን ከመግለፅ በስተቀር፣ ስለ ሟቹ ማንነት ዝርዝር መረጃ አልሰጠም፡፡





   ተቃውሞ የበረታባቸው የደቡብ አፍሪካው ፕሬዚዳንት ጃኮብ ዙማ፤ በገዛ ፈቃዳቸው ስልጣናቸውን ለመልቀቅ ጥያቄ አቅርበዋል በሚል ሰሞኑን በስፋት ሲሰራጭ የሰነበተውን መረጃ ፓርቲያቸው አፍሪካን ናሽናል ኮንግረስ ማስተባበሉን ሮይተርስ ዘገበ፡፡
የአገሪቱን ኢኮኖሚ በቅጡ መምራት አቅቷቸዋል፣ ከባለሃብቶች ጋር በመመሳጠር የአገር ሃብት ይመዘብራሉ በሚል ተቃውሞ ያየለባቸው ፕሬዚዳንት ዙማ፣ ሰሞኑን በተካሄደው የፓርቲው የስራ አስፈጻሚ ኮሚቴ ስብሰባ ላይ ስልጣናቸውን ለመልቀቅ ጥያቄ አቅርበዋል በሚል የተለያዩ ጋዜጦችና ድረገጾች መዘገባቸውን ያስታወሰው ሮይተርስ፤ የፓርቲው ቃል አቀባይ ግን፣ መረጃው ሃሰተኛ ነው ሲሉ ማስተባበላቸውን ጠቁሟል፡፡
“ይህ ፍጹም መሰረተ ቢስና ሃሰተኛ መረጃ ነው!... እንዲህ አይነት ነገር አልተደረገም!” ብለዋል የአፍሪካን ናሽናል ኮንግረስ ፓርቲ ቃል አቀባይ ዚዚ ኮድዋ፣ ጋዜጦቹና ድረገጾቹ ያሰራጩትን ዘገባ ሲያስተባብሉ፡፡
የፕሬዚዳንቱ ፓርቲ በአገሪቱ ፖለቲካ ላይ አለመተማመን እንዲሰፍን አድርጓል፣ ኢኮኖሚውንም አደጋ ውስጥ ከትቶታል በሚል ከፖለቲከኞች ትችት እየተሰነዘረበት እንደሚገኝ ያስታወሰው ዘገባው፣ የአገሪቱ የጸረ ሙስና ኮሚሽንም ፕሬዚዳንቱ የተጠረጠሩበትን ድርጊት እንደሚመረምር ባለፈው ማክሰኞ ማስታወቁን አክሎ ገልጧል፡፡

 ሶማሊያ ከኢትዮጵያ ትሻላለች ተብሏል
    ሰስቴኔብል ዴቨሎፕመንት ሶሊዩሽንስ ኔትዎርክ የተባለ ተቋም በአፍሪካ አህጉር በደስተኝነት ቀዳሚ ናቸው ያላቸውን አገራት ዝርዝር ይፋ ማድረጉን ሲኤንኤን ዘገበ፡፡
አጠቃላይ የአገር ውስጥ ምርት፣ የማህበራዊ ድጋፍ፣ አማካይ ዕድሜ፣ ለሙስና ያለውን አመለካከትና የመሳሰሉትን መስፈርቶች በመጠቀም አገራቱን በደረጃ ያስቀመጠው የተቋሙ ሪፖርት፤አልጀሪያን ከአፍሪካ እጅግ ደስተኛዋ አገር በማለት በቀዳሚነት አስቀምጧታል። ሞሪሽየስና ሊቢያ ሁለተኛና ሶስተኛ ደረጃን የያዙ ሲሆን ሶማሊያ፣ ቱኒዝያ፣ ናይጀሪያ፣ ዛምቢያ፣ ናሚቢያ፣ ኢትዮጵያና ደቡብ አፍሪካ በቅደም ተከተል እስከ አስረኛ ያለውን ደረጃ ይዘዋል፡፡
ከአለማችን አገራት በደስተኛነት የመጨረሻውን ደረጃ ከያዙት አስር አገራት መካከል ስምንቱ አፍሪካውያን ናቸው ያለው ዘገባው፣ እነሱም ማዳጋስካር፣ ታንዛኒያ፣ ላይቤሪያ፣ ጊኒ፣ ሩዋንዳ፣ ቤኒን፣ ቶጎ እና ብሩንዲ መሆናቸውን ጠቁሟል፡፡
ተቋሙ በአለማቀፍ ደረጃ ባደረገው የአገራት የደስተኝነት ሁኔታ ጥናት፣ የመጀመሪያዎቹን 100 ደረጃዎች ከያዙት አገራት መካከል መካተት የቻሉት የአፍሪካ አገራት አምስት ብቻ መሆናቸውንም ዘገባው አክሎ ገልጧል፡፡

   ከ400 አመታት በፊት ከዚህ አለም በሞት የተለየው እንግሊዛዊው ባለቅኔ ዊሊያም ሼክስፒር የራስ ቅል ከመቃብሩ ውስጥ ባልታወቁ ዘራፊዎች መሰረቁ በአርኪዎሎጂስቶች ጥናት መረጋገጡን አጃንስ ፍራንስ ፕሬስ ከትናንት በስቲያ ዘገበ፡፡
እንግሊዛውያን ተመራማሪዎች በስታንፎርድ የቅዱስ ስላሴ ቤተክርስቲያን ውስጥ በሚገኘው የዊሊያም ሼክስፒር መቃብር ላይ ባደረጉት የራዳር ፍተሻ፣ የባለቅኔው የራስ ቅል መቃብሩ ውስጥ እንደሌለ ማረጋገጣቸውን የጠቆመው ዘገባው፣ የመቃብሩ የላይኛው ክፍልም ከረጅም አመታት በፊት ተከፍቶ እንደነበር የሚያሳይ ምልክት መገኘቱን ገልጧል፡፡
በዚሁ ምልክት ላይ በተደረገ ምርመራ፣ የራስ ቅሉ የተዘረፈው በ18ኛው መቶ ክፍለ ዘመን ሳይሆን እንደማይቀር መገመቱ የተነገረ ሲሆን፣ የራስ ቅሉ መጥፋት የታወቀው ባለቅኔው ከዚህ አለም በሞት የተለየበትን 400ኛ አመት በማስመልከት ዶክመንተሪ ፊልም በሚሰራበት ወቅት መሆኑንም አስረድቷል፡፡
ሼክስፒር ከሚወዳት ባለቤቱ አና ሃትዌይ ጎን መቀበሩን ያስታወሰው ዘገባው፣ የመቃብር ስፍራው ለረጅም አመታት በበርካታ የባለቅኔው አድናቂዎች ሲጎበኝ የኖረ ትልቅ ስፍራ እንደነበርም አክሎ ገልጧል፡፡

 በመላ አውሮፓ እጅግ የከፉ ጥቃቶችን ለመሰንዘር ዝቷል
      ባለፈው ማክሰኞ በቤልጂየም መዲና ብራስልስ በፈጸማቸው የሽብር ጥቃቶች ከሰላሳ በላይ ሰዎችን ለሞት፣ ከ300 በላይ የሚሆኑትን ደግሞ ለመቁሰል አደጋ የዳረገው አሸባሪው ቡድን አይሲስ፣ ገና ምን አይታችሁ፤ አውሮፓንና ሊያጠፉኝ የተነሱ አገራትን በሽብር በማናወጥ እጅግ የከፋ ጥፋት አደርሳለሁ ሲል መዛቱ ተዘግቧል፡፡
የሽብር ቡድኑ ባሰራጨው መግለጫ፣ በእኔ ላይ ተባብረው በተነሱ የአውሮፓ አገራትና አጋሮቻቸው ላይ ሌሎች የከፉ የሽብር ጥቃቶችን እንዲፈጽሙ አደገኛ ፈንጂዎችንና የጥፋት መሳሪያዎችን ያስታጠቅኳቸው ወታደሮቼ፣ በቀጣይም ገና ብዙ ጥፋት ያደርሳሉ ሲል መዛቱን ዘ ኢንዲፔንደንት ዘግቧል፡፡
አይሲስ በህቡዕ ያደራጃቸውና 600 ያህል በከፍተኛ ሁኔታ የሰለጠኑ ወታደሮችን ያቀፉ ከመቶ በላይ የሽብር ህዋሶች በተለያዩ የአውሮፓ አገራት ውስጥ ከባድ ጥቃት ለመፈጸም በተጠንቀቅ ላይ እንደሚገኙ የዘገበው ዘ ሰን በበኩሉ፣ ጽንፈኛው ቡድን ለንደንና በርሊንን ጨምሮ በታላላቅ የአውሮፓ ከተሞች ከፍተኛ ጥቃት የሚያደርሱ ጥቃቶችን ለመሰንዘር ተዘጋጅቷል ብሏል፡፡
የአይሲስ ከፍተኛ አመራር በየአገራቱ ለሚገኙት የሽብር ህዋሶቹ መሪዎች የሽብር ጥቃቶችን ለመፈጸም ዝግጅታቸውን እንዲያጠናቅቁና ጥቃቶቹ የሚፈጸሙባቸውን ቦታዎችና አፈጻጸማቸውን ሲመርጡ፣ በአህጉሪቱ ከፍተኛ ቀውስ የሚፈጥሩና የብዙዎችን ህይወት የሚቀጥፉ መሆናቸውን ከግምት ውስጥ በማስገባት መሆን እንዳለበት መመሪያ መስጠቱንም ዘገባው ገልጧል፡፡
የብራስልሱን አሰቃቂ የሽብር ጥቃት ተከትሎ የአውሮፓ አገራት የደህንነት ሃይላቸውን በማጠናከር ተጠምደው መሰንበታቸውን የዘገበው ቢቢሲ፣ ፈረንሳይ ተጨማሪ 1 ሺህ 600 ፖሊሶችን በባቡር ጣቢያዎች፣ በአውሮፕላን ማረፊያዎችና በድንበር አካባቢዎች ማሰማራቷን ጠቁሞ፣ አስቸኳይ ስብሰባ የጠሩት የእንግሊዙ ጠቅላይ ሚኒስትር ዴቪድ ካሜሩንም የአገሪቱ የደህንነት ቁጥጥርና የፖሊስ ሃይል እንቅስቃሴው በከፍተኛ ሁኔታ እንዲጠናከር ማዘዛቸውን ጠቅሷል። ጀርመንና ሌሎች የአውሮፓ አገራትም ዜጎቻቸውን ከአይሲስ ሊፈጸም ከሚችል የሽብር ጥቃት ለመከላከል የተጠናከረ እንቅስቃሴ በማድረግ ላይ እንደሚገኙ ዘገባው አክሎ ገልጧል፡፡

 በፍራንሴስ ዊሊያምስ ተዘጋጅቶ የታተመው “Understanding Ethiopia: Geology and Scenery” የተሰኘ መጽሐፍ የፊታችን ሀሙስ ከምሽቱ 11 ሰዓት እስከ 12 ሰዓት ተኩል 22 ማዞሪያ ድንበሯ ሆስፒታል አጠገብ በሚገኘው ሮድ ራነር ባር እና ሬስቶራንት ውስጥ ይመረቃል፡፡
መጽሐፉ ያለምንም ሙያዊ ቋንቋ፣ ለሁሉም ሰው በሚገባ መልኩ እንደተሰናዳ የተገለፀ ሲሆን በብዙ ባለቀለም ካርታዎችና ፎቶግራፎች የደመቀና የተሞላ እንደሆነም ተጠቁሟል፡፡
የምረቃ ሥነስርዓቱን መግቢያ ንግግር የሚያደርጉት በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ስኩል ኦፍ ኸርዝ ሳይንስ መምህር ፕሮፌሰር ገዛኸኝ ይርጉ ሲሆኑ መጽሐፉ በዕለቱ በ20 ዶላር ወይም በ400 ብር ገደማ ለሽያጭ እንደሚቀርብ ታውቋል፡፡ የምረቃ ሥነስርዓቱን የአዲስ አበባው “ኢትዮጵያን ኳድራንትስ” እና የአዴላይድ ዩኒቨርሲቲ፣ኸርዝ ሳይንስ መምህሩ ፍራንሴስ ዊሊያምስ በመተባበር እንዳዘጋጁት ለማወቅ ተችሏል፡፡

Saturday, 26 March 2016 11:40

የኪነት ጥግ

(ስለ ተዋንያን)
ድራማን በተመለከተ ተሳስቻለሁ፡፡ ድራማ የሚባለው ተዋንያኑ ሲያለቅሱ ይመስለኝ ነበር፡፡ ድራማ ግን ተመልካቹ ሲያለቅስ ነው፡፡
ፍራንክ ካፕራ
ሰዎች በአንድ ነገር ብቻ መታወስ ለምን እንደሚይናድዳቸው ይገባኛል፡፡ ብዙዎቹ ተዋንያን ግን በምንም ነገር አይታወሱም፡፡ እኔ ለዚያ ደንታ የለኝም፡፡
ጁሊ ዋልተርስ
ተዋንያን የለውጥ ሃዋርያ ናቸው፡፡ አንድ ፊልም፣ ቲያትር፣ ሙዚቃ ወይም መጽሐፍ ልዩነት ይፈጥራል፡፡ ዓለምን ሊለውጥ ይችላል፡፡
ኢላን ሪክማን
የምጫወተው ገፀባህርይ ባለፈው ማክሰኞ ቁርሱን ምን እንደበላ የማውቅ ዓይነት ተዋናይ አይደለሁም፡፡
ሊያም ኒሰን
ተዋናዩ ዩኒቨርስን በእጁ መዳፍ ላይ መፍጠር መቻል አለበት፡፡
ሎውረንስ ኦሊቪዬር
ተዋናይ፤ ስለእሱ እያወራችሁ ካልሆነ በቀር የማያዳምጣችሁ ሰው ማለት ነው፡፡
ማርሎን ብራንዶ
ግሩም ተዋናይ መሆን ቀላል አይደለም፡፡ ሰው መሆን ደግሞ የበለጠ ከባድ ነው፡፡ ዕድሜዬ ከመጥለቁ በፊት ሁለቱንም ለመሆን እሻለሁ፡፡
ጄምስ ዲን
እያንዳንዱ ተዋናይ ሁሉንም ሰው ለመሆን ይሻል - ሁሉንም ገፀ ባህርያት መጫወት፡፡
ኬይሌ ቻንድለር
ሁሉም ተዋንያን ተንኮለኞች ናቸው፡፡ ሁላችንም ችግር ፈጣሪዎች ነን - አሰቃቂ፣ ትኩረት ፈላጊ ህፃናት፡፡ “እኔ…እኔ…እኔን ተመልከቱኝ” የምንል።
ሴይና ጉይሌሪ
እኔ ተዋናይ ነኝ፤ ኮከብ አይደለሁም፡፡ ክዋክብቱ በሆሊውድ የሚኖሩና የልብ ቅርጽ ያለው የመዋኛ ገንዳ ያላቸው ናቸው፡፡
አል ፓቺኖ
ግሩም ዳይሬክተር፤ ተዋናዩ ክንፍ አውጥቶ የመብረር ብርታት የሚያጐናጽፈውን ከባቢ ይፈጥራል፡፡
ኬቪን ቤከን
ሁለት ዓይነት ተዋንያን አሉ፡- ዝነኛ መሆን አልንፈልግም የሚሉና ውሸታሞች፡፡
ኬቪን ቤከን

       ዋና አሰልጣኝ ብርሃኑ ግዛው የኢትዮጵያ ሴቶች ብሄራዊ ቡድኑ ወደ አፍሪካ ዋንጫ ለማለፍ ጥሩ እድል እንዳለው ያምንበታል፡፡ ዛሬ በአዲስ አበባ ስታድዬም የመልስ ጨዋታ ያደርጋሉ፡፡ ከሁለት ሳምንት በፊት በአልጀርስ ተደርጎ በነበረው ጨዋታ ሉሲዎቹ በአልጄርያ አቻቸው 1ለ0 መሸነፋቸው ይታወሳል፡፡ ዛሬ ጥሎ በማለፍ ወደመጨረሻው የማጣርያ ምእራፍ ለመሸጋገር 2ለ0 እና ከዚያም በላይ ማሸነፍ አለባቸው፡፡
     አልጄርያ በሴቶች እግር ኳስ ጥሩ ደረጃ ላይ እንደሆነች ለስፖርት አድማስ የተናገረው ዋና አሰልጣኝ ብርሃኑ ግዛው፤ በሰሜን አፍሪካዊቷ አገር የሴቶች እግር ኳስ በተናጠል  ፌደሬሽን፤ ሊግ አስተዳደር፤ ስታድዬሞች መከናወኑ በረጅም ግዜ በተዘረጉ እቅዶች የሚካሄድ መሆኑን ልንማርበት ይገባል ሲል ያሰምርበታል፡፡ በአልጄርያ እግር ኳስ በሀ 17 እና በሀ 20 የሴቶች እግር ኳስ መንቀሳቀሱን እንደተምሳሌት በመውሰድም በኢትዮጵያ ልንሰራበት ይገባል ብሎም አስተያየት ይሰጣል፡፡
ሉሲዎቹ ዛሬ የሚገጥሙት የአልጄርያ ብሄራዊ ቡድን 12 ፕሮፌሽናል ተጨዋቾች እንዳሉበት የሚገልፀው ዋና አሰልጣኝ ብርሃኑ፤  በመጀመርያው ጨዋታ 1ለ0 መሸነፋቸው የሉሲዎችን ጥንካሬ እንደሚያሳይ አስገንዝቦ፤  በመልሱ ጨዋታ በሜዳችን፤ በአየራችን እና በደጋፊያችን ፊት ውጤቱን ለመቀልበስ ነው ተስፋ የምናደርገው በሁላችንም ትግልና ጥንካሬ ነው ሲል ይናገራል፡፡ የመልሱን ጨዋታ በከፍተኛ ጥንቃቄ  የምናደርገው ይሆናል ያለው ዋና አሰልጣኙ፤ ጥሩ ዝግጅት ማድረጋቸውን፤ በሜዳቸው ብዙ ዋጋ ሊያከፍል የሚችል ግብ እንዳይቆጠር መስራታቸውን  ለስፖርት አድማስ አብራርቷል፡፡
የሉሲዎቹ አባላት በስነምግባራቸው ጥሩ ደረጃ ላይ መሆናቸውን የሚገልፀው ዋና አሰልጣኝ ብርሃኑ ግዛው፤  እንደ ሎዛ አበራ አይነት ወጣትና ምርጥ የአጥቂ መስመር ተጨዋች፤ በአፍሪካ ዋንጫ ልምድ ያላቻቸው አጥቂዋ ረሂማ ዘርጋው፤  ግብ ጠባቂዋ ዳግማዊትና አምበሏ ብርቱካን ገብረክርስቶስ ቡድኑን በመምራት ባላቸው ከፍተኛ ሚና ደስተኛ ነው፡፡ በአጠቃላይ ቡድኑ በታዳጊ፤ በወጣት እና በአንጋፋ ተጨዋቾች ስብስብ የተገነባ መሆኑ ጠንካራ እንደሚያደርገውም ለስፖርት አድማስ በሰጠው ቃለምልልስ ዋና አሰልጣኝ ብርሃኑ ግዛው ተናግሯል፡፡ ለወደፊቱ ብሄራዊ ቡድኑ ለተጨዋቾቹ በቂ ጥቅም ሆነው የሚታዩ ማበረታቻዎችን፤ ለዝግጅት የሚያግዙ በቂ የወዳጅነት ጨዋታዎችን በማዘጋጀት ፌደሬሽኑ የቡድኑን ጥንካሬ ለማጎልበት መንቀሳቀስ አለበትም ሲል መልዕክቱን ያስተላልፋል፡፡ ስፖርት አድማስ ከሉሲዎቹ ዋና አሰልጣኝ ብርሃኑ ግዛው ጋር ያደረገው ልዩ ቃለምልልስ ከዚህ በታች የቀረበው ነው፡፡
በስፖርት ላይ የሚያተኩር ልዩ እና ፈርቀዳጅ መፅሃፍ አሳትመሃል ቃለምልልሱን በሱ ስንጀምርስ
አዎ፤ ልክ ነህ፡፡ በስፖርት ብቻ ሳይሆን በህይወት ታሪኬ ላይ የሚያተኩር መፅሃፍ ነው፡፡ “ከስደት መልስ እስከ ብሄራዊ ቡድን አሰልጣኝነት” በሚል ርእስ የተዘጋጀ ነው፡፡ ብዙ ወጣቶች በስደት ህይወት እንደሚባክኑ የሚታይ ቢሆንም በመፅሃፌ ከስደት ህይወት ተመልሶ ስኬት ማግኘት እንደሚቻል ለማስረዳት ሞክርያለሁ፡፡ በተጨማሪም መፅሃፉ በግል ህይወቴ ብቻ ሳይሆን ከስፖርቱ ጋር በተያያዘ እግር ኳስን በተጫዋችነት ከዚያም በአሰልጣኝነት እንዴት እንዳሳለፍኩ፤ ወደስልጠና ሙያ ለመግባት በምን አይነት ስነምግባር በርካታ ውጣውረዶችን እንዳለፍኩ የሚያወሳ ነው፡፡
የስፖርት መፅሃፍ አዘጋጅቶ ለገበያ ማቅረብ የተለመደ አይደለም፤ አንተን ምን አነሳስቶህ ነው?
መፅሃፉን ሳሰትም ዋናው ዓላማዬ የህይወት ተመክሮዬና በስፖርቱ ያሳለፍኩትን ጥረትና ልምድ ለህዝብ እንዲደርስ በማሰብ ነው፡፡ በመጀመርያው እትም የመፅሃፉ ብዛት ያን ያህል አርኪ አልነበረም፡፡ 1500 ኮፒ ብቻ ነበር ያሳተምኩት። ወዲያው ለገበያ እንደቀረበ ወርም ሳይሞላ ነበር ያለቀው፡፡ አሁን በቅርብ ጊዜ ሁለተኛ እትም ለማሳተም እየተንቀሳቀስኩ ነው። እንደእቅዴ ከሆነ ሁለተኛውን እትም በ4ሺ እና በ5ሺ ኮፒ ለማሳተም ነው፡፡
መፅሃፉን በምን ዓላማ ነው አሳተምከው፤  ታላላቅ አትሌቶችና የእግር ኳስ ባለታሪኮች በዚህ ረገድ ብዙም ሲንቀሳቀሱ አይታይም፤ ማንስ ነው መፅሃፍ የማዘጋጀት ሃላፊነት ያለበት ጋዜጠኞች ወይንስ ባለታሪኮቹ ስፖርተኞች?
እኔ እንደሚመስለኝ  ባለቤቱ ራሱ እንደመሆኑ ሃላፊነቱ የስፖርተኛው ነው፡፡ ያለፍክባቸውን የስፖርት ተመክሮዎች፤ የሰራሃቸውን ታሪኮች አስተማሪነት እንዳላቸው ካመንክበት በራስህ ጥረት ልታደርገው የሚገባ ስለሆነ ነው፡፡ ግን በስራ ዘመንህ ታሪኮችን በአግባቡ መሰነድ፤ በማስታወሻ እየከተብክ ማኖር እና ከተለያዩ አቅጣጫዎች በማገናዘብ አዘጋጅተህ ተግባራዊ ልታደርገው የምትችል ነው፡፡ እኔ መፅሃፉን ያሳተምኩት ልጄን ከወለድኩ በኋላ ስለሆነ ከዚያ እንደሁለተኛ ልጄ ነው የቆጠርኩት፡፡ መፅሃፍ ታሪክን የሚያስቀምጥ ነው፡፡ የሚመጣ ትውልድ ሊማርበት የሚችል ነው፡፡ ከታሪክህ ብዙ ስፖርተኛ አንብቦ ሊማር የሚችለው ብዙ ቁምነገር መኖሩን መገንዘብ አለብህ፡፡ በእኛ አገር ስፖርተኞች የተለመደው ጡረታ ከተወጣ በኋላ መፃፍ ነው፡፡ ነገር ግን እኔ እንደማስበው በስራ ዘመንህ፤ በህይወት ላይ ጉልበት እና ሞራል እያለህ በምታልፍባቸው የስራ ውጣውረዶች እና ጎዳናዎች ያሉህን ተመክሮዎች እየተገነዘብክ በየጊዜው መፃፉ አስፈላጊም ተገቢም ነው፡፡
እንግዲህ አንተ ባለህ የስራ ልምድ አብዛኛውን ድርሻ የሚወስደው በሴቶች እግር ኳስ ላይ ያለህ ተመክሮ ነው፡፡ ‹‹ከስደት መልስ እስከ ብሄራዊ ቡድን አሰልጣኝነት” በሚለው መፅሃፍህ በሴቶች እግር ኳስ ዙርያ ምን ምን ተወስቷል፡፡
በሴቶች እግር ኳስ አሰልጣኝነት መስራት ከጀመርኩ እንግዲህ 17 ዓመታት ተቆጥረዋል፡፡ በ17 ዓመት ውስጥ  የሴቶች እግር ኳስ ሲጀመር ማለትም ገና ሲፀነስ ነበርኩ፤ ከዚያም እርግዝናው ላይ ምጡ ላይም አለሁበት፡፡ ከዚያም ተወልዶ ዳዴ ብሎ ማደግ ሲጀምርም እየሰራሁበት ነው፡፡
የሴቶችን እግር  ኳስ ከጅምሩ እዚህ አገር ውስጥ ብዙም ተቀባይነት ስላልነበረው ከመጀመርያው ይህን ተቀባይነት ለማግኘት ብዙ ጥረት ማድረግ ነበረብን፤ ይገርምሃል ያኔ ከ17 ዓመታት በፊት ሜዳ ለወንድ ተጨዋቾች ሲለቀቅ ለሴት ኳስ ተጨዋቾች የሚለቅ ሁሉ አልነበረም፡፡ በሌላ በኩል የፋይናንስ እጥረት ነበር፡፡ ያኔ በገንዘብ በኩል ያለብንን ችግር ለመቅረፍ ይገርምሃል ሆያ ሆዬ፤ አበባየሁሽ እየጨፍርን ገቢ ለማግኘት እንጥር ነበር፤ ይህ እንግዲህ ከ14 ዓመታት በፊት ነው፡፡ ከሆያ ሆዬ እና ከአበባየሁሽ ጭፈራ በኋላም እኛ አሰልጣኞቹ እና ወጣቶቹ ሴት እግር ኳስተጨዋቾች የራሳችንን እጣ እንደበግ እና ሌሎች ሽልማቶች ያሉበትን ሎተሪ አዘጋጅተን እና ተዟዙሮ በመሸጥ ገንዘብ ለማግኘት ሁሉ ሰርተናል፡፡ እነዚህን ገቢ የማሰባሰብ ተግባራት በመጀመርያ ጃንሜዳ አካባቢ ጀምረነው ከዚያም፤ ወደ ፒያሳ መርካቶ ኮተቤ እየሄድን የምንሰራቸው ነበሩ፡፡ ወደ ተለያዩ ክልሎችም እየተንቀሳቀስን ገንዘብ ሰብስበናል፡፡ በእነዚህ እንቅስቃሴዎች የምናገኘውን ገንዘብ የምንሰበስበው ከልምምድ በኋላ ነበር፡፡ ድንችና ፓስታ ቀቅለን ተጨዋቾቻችንን እየመገብን ሁሉም ከየተሰማራበት አቅጣጫ የሰበሰበውን እንረከባለን፡፡ አምበሎች አማካኝነት የተሰበሰበው ገንዘብ ኳስ እና፤ ማሊያ የተለያዩ ትጥቆች ይገዙበታል፡፡ በአዲስ አበባ ከፍተኛ ዲቪዚዮን እና አንደኛ ዲቪዚዮን ውድድሮች ከፍለን በመመዝገብ ተሳትፎ ማድረግ እየቻልን መጣን። በእነዚህ ውድድሮች ለመሳተፍእስከ 1000 ብር መክፈል ነበረብን። ከ14 ዓመታት በፊት ይህ ብዙ ገንዘብ ነው፡፡ ለምሳሌ አንድ ሰው አንገቱ ላይ የወርቅ ሃብል አጥልቋል፡፡ ሰው ወርቁን ሲያይ ሊደንቀው ይችላል፡፡ ግን መጀመርያ ወርቁ የመጣበትን ወርቁ የተፈተነበትን፤ ወርቁ እንዴት ተቃጥሎ እንደመጣ የሚያቀው ወርቁ ራሱ ነው፡፡ ግን ከፈተና የወጣ  ሁል ጊዜ ማማር ይችላል። እኛ በሴቶችእግር ኳስያሳለፍነው ተመክሮ እንደዚህ የሚገለፅ ነው፡፡ የመጽሐፌም ይህን የመሰሉ ታሪኮች ተነስተዋል፡፡
በፌደሬሽኑ በኩል ያን ግዜ የምታደርጉትን እንቅስቃሴ የሚደግፍ አሰራር አልነበረም እንዴ
እንግዲህ ዓለም አቀፉ  የእግር ኳስ ማህበር በሴቶችእግር ኳስ ላይ ማተኮር የጀመረው ከ25 ዓመታት በፊት እንደሆነ ታውቃለህ፤ እናም እኛ በሴቶች እግር ኳስ መንቀሳቀስ ስንጀምር ከፊፋ የሚላክ ገንዘብ ቢኖርም በፌደሬሽኑ በኩል የነበረው ትኩረት ደካማ ስለነበር የሚመጣው የበጀት ድጋፍ ለወንዶቹ ውድድሮች ነበር የሚሰራጨው፡፡ እንደምታውቀው ፊፋ ለአባል ፌደሬሽኖች ከሚያበረክታቸው የገንዘብ ድጋፎ ለሴቶችና ወጣቶች የእግር ኳስ እንቅስቃሴ እስከ 250ሺ ዶላር በየውድድር ዘመኑ ይሰጣል፡፡ ይህ በጀት ወደ ውድድሮች ነው የሚሄደው በአንድ ታዳጊ አገር አቅሙ ባለመኖሩ የሚያስደነግጥ አይደለም፤ እኛ ስንጀምረው  በሴቶች እግር ኳስ አሰልጣኝነት የምንሰራ ባለሙያዎች ጥቂት ነበርን፡፡ ጋሽ ይተፋ፤ ያሬድ ቶሌራ፤ ደረጀ ነጋ፤ ፍቃዱ ማሙዬ እና እኔ በማሰልጠን እንሰራ በነበርነበት ጊዜ በጃንሜዳ አካባቢ የተወሰነ ነበር እንቅስቃሴያችን፡፡ ደረጃ ብቻ ነበር የካ አካባቢ ይሰራ ነበር። እኔ ማሰልጠኑን ስጀምር በወንዶችእግር ኳስ ነበር ለምሳሌ እነ አሉላ ግርማን የመሳሰሉ ተጨዋቾች ባፈሩ ፕሮጀክቶች እሰራ ነበር፡፡ ከግዜ በኋላ ግን በሴቶችእግር ኳስ ብዙ የሚሰራ ባለመኖሩ ወደዚያ መስክ ለመዞር በመወሰን የገባሁበት ነው፡፡ ብዙ ሙያተኞች በዚህ ውሳኒያችን ተገርመው ይንቁንም ነበር። በጃንሜዳ  የአዲስ አበባ ከፍተኛ ዲቪዝዮን በሚባል መደበኛ ውድድር ቡድኖቻችንን ይዘን እንሳተፍ ነበር፡፡
ብዙ ዓመታትን በጃሜዳ የዲቪዚዮን ውድድሮች ካሳለፍን በኋላ የክልል ሻምፒዮናዎች መካሄድ ጀመሩ፤ ከዚያም ፕሪሚዬር ሊግ መጣ፡፡ የሚገርምህ በከፍተኛ ዲቪዝዮን ይጫወቱ የነበሩ ልጆች ኳስ ብዙም ገቢ ስለማይፈጥርላቸው ወደ አረብ አገራት መሰደድን ሁሉ የሚመርጡበት ሁኔታ ነበር፡፡ ፕሪሚዬር ሊግ ሲጀመር ግን  የሴቶች እግር ኳስ ከስደት የተሻለ ህይወት እና ገቢ የሚገኝበትን እድል ስለሚፈጥር ሁኔታው ሊቀየር ችሏል፡፡
እንግዲህ ባለፉት 14 ዓመታት የሴቶችእግር ኳስ ያለፉባቸውን ውጣውረዶች በመጠኑ ዳስሰሃቸዋል፡፡ አሁን ያለበትን ደረጃ የምትገልፀው እንዴት ነው
 አሁን የሴቶች እግር ኳስን  ህብረተሰቡ ተቀብሎታል፤ ቤተሰብምም ተቀብሎት የሚደግፈው ሆኗል፤ ከወንዶች የእግር ኳስ እንቅስቃሴ እኩልም ትኩረት እየተሰጠው ነው፡፡ አሁን ለምሳሌ በክፍለ ከተማ ደረጃ እንኳ የወንዶችም የሴቶችም ቡድኖች እየተመሰረቱ ናቸው፡፡ እግር ኳሱን እያሻሸለው ያለ አቅጣጫ ነው፡፡ ክለቦችም ከመቼውም ጊዜ በላቀ ሁኔታ ትኩረት ሰጥተው እየሰሩበት ናቸው፡፡ ድሮ ቡና ጊዮርጊስ ብለን ስለቡድኖቹ የምንሰማው በወንዶች ብቻ ነበር፣ አሁን ደግሞ በሴቶችም የሚታይ መደበኛ ተግባር እየሆነ ነው፡፡ በፕሪሚዬር ሊግ ደረጃ ክለቦች የየራሳቸውን ቡድኖች በማቋቋም መወዳደራቸው የሚያደስት ቢሆንም ግን አንዳንድ ክፍተቶች አሉ በታዳጊዎች ደረጃ እየተሰራ….
ይቅርታ ብርሃኑ የብሄራዊ ቡድን ዋና አሰልጣኝ እንደመሆንህ ያሉትን ክፍተቶች በግልፅ ልትናገራቸው ያስፈልጋል..
ልክ ነህ፡፡ ለሴቶች እግር ኳስ መለወጥ እና ማደግ ከፍተኛ መስዕዋትነት ከፍዬ የደረስኩበት ደረጃላይ የወደፊቱን ተስፋ የሚያደበዝዝ እና እድገቱን የሚያንቀራፍፍ ሁኔታ ከታዘብኩ እተቻለሁ፡፡ ክለቦች በፕሪሚዬር ሊግ ደረጃ የሴቶች ቡድኖችን መስርተው መወዳደር ሲጀምሩ ለተጨዋቾቻቸው የወንድ ትጥቆችን በማቅረብ፤ አነስተኛ በጀት በመመደብ ነበር፡፡ አሁን ግን ሁሉም ክለቦች በሴት ቡድኖቻቸው ምስረታ የእኔነት ስሜት በማዳበር መንቀሳቀሳቸው ትልቅለውጥ ይመስለኛል። ይህ ብቻውን ግን በቂ አይደለም፡፡ አሁን አንዳንድ ክለቦች የመሰረቷቸውን ቡድኖች ያለበቂ ምክንያት እያፈረሱ ናቸው፡፡ ለሴቶች እግር ኳስ ክብር የማይሰጡ ክለቦች አሉ፡፡ ለወንዶች  ከፍተኛ በጀት እየመደቡ የሚንቀሳቀሱ አንዳንድ ክለቦች የሴት ቡድኖቻቸውን እንደዘበት የሚያፈርሱት አካሄድ በፍፁም ልክ አይደለም፡፡ ሴቶች እኮ በየትኛውም መስክ ዋንኛ አካላት ናቸው። ምናልባት በየክለቡ ሴት አመራሮችም ይኖራሉ እና ታድያ የተመሰረተ ክለብን ማፈራረስ እና መበታተን ለምንድነው፡፡ ቡድኖቻቸውን ካፈረሱ ክለቦች መካከል  ወላይታ ዲቻና መድን ይጠቀሳሉ፡፡ በወላይታ ዲቻ በኩል ክልሉ፤ በመድን በኩል የክለቡ አስተዳደር ይህ ተግባር ለምን ዝም እንዳሉት አይገባኝም፡፡ በሌላ በኩል እንደወልዲያ ከነማ አይነት ክለቦች የሴቶች ቡድን እንዲመሰርቱ ፌደሬሽኑ ለምን አያስገድድም፡፡ የተመሰረቱ ቡድኖችን ማፍረስ፤ ከእነጭራሹ በሴቶች እግር ኳስ ያለመስራት ሁኔታዎች መጥፎ አዝማሚያዎች ይመስሉኛል፡፡ በትጋት በሚሰሩ ክለቦች ላይ የሚዛመቱ ችግሮች ስለሚሆኑም ስጋት አለኝ፡፡ የግንዛቤ እግር በአመራሮች ላይ ይታያል፡፡ ጠንካራ የሴቶች እግር ኳስ እንቅስቃሴን በሚያሳዩ እንደ ንግድ ባንክ፤ ደደቢት እና ዳሸን፤ ቡናና ጊዮርጊስ ያሉ ክለቦች ያለው ችግር ደግሞ በወንዶቹ የሚሰጡትን ትኩረት ያህል አለመስራታቸው ነው፡፡ በተለይ በታዳጊ ደረጃ ወርደው የሚሰሩ ክለቦች አለመኖራቸውነው የሚያሳስበኝ፡፡ በታዳጊ ደረጃመስራት ለነገው መሰረት መጣል ነው፡፡
በአጠቃላይ ክለቦች በሴቶች እግር ኳስ ታዳጊ ቡድኖችንም አቋቁመው ለመስራት መትጋት ይኖርባቸዋል፡፡ ከዚህ በተጨማሪ በፕሪሚዬር ሊጉ ተወዳዳሪ በሆኑ ክለቦች ለሴት ተጨዋቾች ተመጣጣኝ ደሞዝ የሚከፈልበት አሰራር መፈጠር ይኖርበታል፡፡ በእርግጥ በታዳጊዎች ላይ መስራት ብቻን መፍትሄ ላይሆን ይችላል፡፡ ከፕሪሚዬር ሊጉ ባሻገር የታዳጊ ውድድሮች ያፈልጋሉ፤ በስልጠና የሚሰሩ ብቁ ባለሙያዎችም ሊኖሩ ግድ ይላል፡፡ ለምሳሌ ባለሙያዎችንም ማብቃት የፌደሬሽኑ ስራ መሆን አለበት፤ ለምሳሌ እግር ኳስን ያቆሙ የቀድሞ ሴት ተጨዋቾች በየቤታቸው ተቀምጠዋል እነሱን ወደ ስልጠናው መስክ ለማስገባት የሚያስችሉ የአቅም ግንባታ ስልጠናዎች መፈጠር አለባቸው፡፡ ከዚያቀጥሎ ክለቦች ብቁ ባለሙያዎችን ይዘው የታዳጊ ቡድኖችን መስርተው መንቀሳቀስ ሲጀምሩ ውድድሮችን ለመፍጠር እና ለማካሄድ ብዙ የሚቸግር አይሆንም፡፡
በግሌ እምነት በሴቶችእግር ኳስ  በሁሉም ክለቦች ያሉት እንቅስቃሴዎች የሚያበረታቱ ቢሆንም በደደቢት እና በንግድ ባንክ ክለቦች እንዲሁም በዳሸን ያሉ ተግባራት እንደ ተምሳሌት ሊጠቀሱ የሚችል ነው፡፡ በእነዚህ ክለቦች ለሴት ተጨዋቾች ከወንዶቹ እኩል በቂ ትኩረት እየተሰጠ ነው፡፡ ተመጣጣኝ የደሞዝ ክፍያም እየተገበሩ ናቸው፡፡ በትጥቅ አቅርቦት፤ በአስተዳደር ትኩረት፤ በደሞዝ መሻሻሎች መኖርአለባቸው። እነዚህን አሰራሮች ሌሎች አንጋፋ ክለቦችም መከተል አለባቸው፡፡

ከዕለታት አንድ ቀን አንድ አዕምሮውን ነካ ያደርገዋል የሚባል ሰው ቀን በጠራራ ፀሐይ ወደ አንድ የስልክ እንጨት (ምሰሶ) ይሄዳል፡፡ ከዚያም እንደ ስልከኛ ምሰሶው ላይ እግሩን አጠላልፎ መውጣት ይጀምራል፡፡
ሰው ምን ሊያደርግ ነው እያለ ዙሪያውን መክበብ ጀመረ፡፡ ዙሪያውን የከበበውን ሰው ያየ መንገደኛ ሁሉ ወደ ስብስቡ ተቀላቀለ፡፡ የሁሉም ሰው ጥያቄ፤
“ምን ሊያደርግ ይሆን?” የሚል ሆነ፡፡
ሰውየው መውጣቱን ቀጠለ፡፡ ህዝቡም መሰብሰቡን ቀጠለ፡፡
ከፊሉ - “ይሄ ሰውዬ ጫፍ ከደረሰ በኋላ ሊወረወር ነው፡፡ በጊዜ እናስወርደው” አለ፡፡
ከፊሉ - “ለማንኛውም ፖሊስ ብንጠራ ይሻላል”
ሌላው - “ፖሊስ ቢመጣ ምን ሊያደርግ ይችላል፡፡ በገመድ አይጠልፈው”
ሌላው - “ግዴላችሁም አንድ ሰው ተከትሎት ይውጣ”
“ተከትሎት ወጥቶ በእርግጫ ቢለውስ ዕብድ አይደለ እንዴ?”
“እባችሁ ምንም አይሆን፤ ዝም ብለን የሚያደርገውን እንይ”
“ለምን አንጠይቀውም?”
“ምን ብለን ልንጠይቀው ነው፤ እኛ ቴሌ ኮሙኒኬሽን አደለን”
“ለምን ለሚመለከተው መስሪያ ቤት አንነግርም”
“መሥሪያ ቤቱ ንብረቴ ነው ካለ እራሱ ይምጣ እንጂ እኛ ምን ቤት ነን?”
ዕብዱ ሰው መውጣቱን ቀጠለና ጫፍ ደረሰ፡፡
ቀጠለና ከኪሱ እስክሪቢቶና ወረቀት አወጣ፡፡
ታች ያለው ሰው ግምቱን አወጋ-
“ይሄዋ ኑዛዜውን እየፃፈ ነው”
“ዕብድ ደሞ ምን ኑዛዜ ይኖረዋል?”
“ምን ይታወቃል? ሰውኮ ሊሞት ሲል የሚናገረው ነገር ይበዛል”
“እባክህ፤ መንግሥትን ሊሳደብ ይሆናል”
“መንግሥት ለመሳደብ ምሰሶ ጫፍ ላይ መውጣት አለብህ እንዴ?”
ዕብዱ ሰው ጽሑፉን ጨረሰ፡፡ በፕላስተር ምሰሶው ጫፍ ላይ ለጠፈው፡፡
እየተንሸራተተ ወደ መሬት ወረደ፡፡
ታች ከተሰበሰበው ህዝብ አንዱ፤
“ምን ብለህ ጽፈህ ነው የለጠፍከው?” አለና ጠየቀው፡፡
ዕብዱ ሰውም
“ወጥቶ ማየት ነዋ!” ብሎ ሄደ፡፡
ከህዝቡ ማህል አንደኛው፤
“ወጥተን እንየው እንጂ” አለ፡፡
ሁሉም “አንድ ሰው ይውጣ” አለ፡፡
አንድ ጐበዝ ከማህል ወደ ስልክ እንጨቱ ሄደ፡፡
ሁሉ ሰው አበረታታው፡፡ “ጐበዝ ውጣ!” “ቀጥል ጀግናው!” “ይሄ ነው ወንድ!” “ግፋ!”
ሰውየው እግሩን እየሳበ ወጣ ወጣና ጫፍ ደረሰ፡፡ ወረቀቱ ላይ የተፃፈውን አየ፡፡
ታች የለው ህዝብ “አንብብልን!” ብሎ ጮኸ፡፡
ጐበዙ ሰው ጮክ ብሎ አንበበው፤
“የምሰሶው ጫፍ እዚህ ጋ ነው!”
*   *   *
ማንኛውም ሰው ህዝብን እንዳሻው ለመንዳት ከቻለ ሀገር ላይ ችግር አለ፡፡ ያ ሰው ዕብድ ከሆነ ደግሞ የባሰ ችግር አለ፡፡ አሳሳቢ ሆነ ማለት ነው፡፡ ጥርጣሬ ላይ የወደቀ ህዝብ ይዋልላል፡፡ በመንግሥት፣ በተቋማትና በማህበራት ላይ ዕምነት አይኖረውም፡፡ ዕምነት ያጣ ህዝብ ከመምራት ዕምነት የለው የልቡን የሚናገር ተቃዋሚ ህዝብ መምራት ይሻላል ይላሉ ፀሐፍት፡፡
ኢትዮጵያን በተለየ መንገድ ለማሳደግ ህዝብ በአጭበርባሪዎች እንዳይታለል ተቆጣጥሮ ህጋዊነትን ማስከበር ያሻል፡፡ ህዝብ ሙሉ ዕምነት ሊኖረው ያስፈልጋል፡፡
ተቋማቱን አስተማማኝና እርግጠኛ ፍቃደ ልቡና ይለግሳቸው ዘንድ እንዳይመዘበር፣ እንዳይበዘበዝ ጥበቃ ሊደረግለት ይገባል፡፡ ለዚህም የአስተሳሰብ ብልጽግና፣ የግንዛቤ ጥራት፣ የልብ ለልብ መግባባትና የመቻቻል ምንነት በግልጽ የገባው ሊሆን ያሻል፡፡ ከጦርነት ይልቅ ሰላምን የሚመርጥበት ምክንያት ከልምድ ከተማረው በተጨማሪ ወቅታዊ ንቃት እንዲኖረው ያስፈልጋል፡፡
ሙስናን ለመቋቋም እየሰጋን መሆን የለበትም፡፡ መታሠር ያለበት ህገ ወጥ ሰው ከሆነ የፍርድ ቤት ጉዳይ እንጂ የእከሌ ከእከሌ አማራጭ መፍጠር ወይም “አጥፊው ስለበዛ እንተወው” መፍትሔ አይሆንም፡፡ ሁሉም የየድርሻውን ማግኘቱ የፍትሕን መጉላትና መጠንከርን እንደሚያሳይ አለመዘንጋት ነው፡፡ በተለይ በህዝብ ላብ የሚቀልድ ማንም ይሁን ማን ሊተው አይገባም፡፡ በተለይም በልዩ መዋቅር ተሳስሮ ጀርባው ደንደን ያለውን መተው፣ ኮሳሳውን ማጥቃት ለፍትሕ ጐጂ ባህል ነወ፡፡ ይህን የሚያስከብሩ ተቋማት መጠንከር አለባቸው። ይህም ሲባል ተቋማቱ ግዑዝ አይደሉምና የሚመሯቸው ሰዎች በሚሠሩት አምነውና ጠንክረው ይጓዙ ማለታችን ነው፡፡
አበሻ አደባባይ ያምናል፡፡ ለአበሻ ሚዲያ መንግሥት ነው፡፡ ስለሆነም ለማናቸውም ሚዲያ ተጠቃሚ ተአማኒ ነው፡፡ ሚዲያ ላይ የቀረበ፤ አንድም መንግሥታዊ ነው፣ አንድም የታመነ ነው!  ቴሌቪዥን አይቶ፣ ሬዲዮ ሰምቶ የማያውቅ ሰው እንኳ ቢሆን በቴሌቪዥን ታየ፣ በሬዲዮ ተነገረ ካሉት የዕምነቱን ዣንጥላ ይዘረጋል፡፡ በአደባባይ የታየው፣ የተሰማው ነገር ህጋዊ ነው እንደማለት ነው! የዛሬ ዘመን የ “ቢዝነስ” ሁኔታ የደራሲ አቤ ጉበኛን “ጐብላንድ አጭበርባሪው ጦጣን” የሚያስታውሰን ነው፡፡ ለነገሩ የተመዘበረው ብር ብዛት ሲታይ እሰው እጅ ያለው ገንዘብ ኤሎሄ ያሰኛል፣ እንደ ልብ ደረቅ ቼክ መፃፍ፣ ባንክ ውስጥ በቂ ገንዘብ የለውም መባል፤ የወትሮ ነገር ሆኗል፡፡ ዲቪ የደረሰው ቀርቶ ያልደረሰው ይሄዳል በሚባልበት፣ ኮንዶምኒየም የደረሰው ቀርቶ ያልደረሰው ይኖርበታል በሚባልበት፣ ፖለቲካው ግራ ሲያጋባንና የምሁርነት ጥልቀት እያደር እንደ ውሃችን ቱቦ ሲደፈን
“እንተኛም ካላችሁ፣ እንገንደሰው
መኝታ እንደሆነ ቀርቷል ካንድ ሰው”
የሚል ዘፈን በምናቀነቅንበት ሀገር፤ ፖለቲካ ሁሉ የመሬት ጉዳይ ቢሆን ብዙ የሚያስደምም ሁኔታ አይሆንም፡፡ ጠቅላይ ሚኒስትራችን ለምሁራን ታዳሚዎች እንዳሉት፤ “እኛም እናንተም ችግር አለብን፡፡…ህብረተሰቡም እልከኛ ነው”…ይህንን የችግር ሶስት ማዕዘን (Triangular problem) መቼ እንደምንገላገለው ማሰብ ይጠበቅብናል፡፡
ችግሩ ባለቤት እንጂ ሁልቆ መሣፍርት የለውም፡፡ ዘርዝሮ ማየት እንጂ ችግር አለብን ብቻ መፍትሔ አይሆነንም፡፡ “የኤሊት ግሩፕ ቱጃር እየፈጠርን መጓዝ አንችልም” ያሉት ግን ሊሰመርበት የሚገባ ሀቅ ነው፡፡ “የመላዕክት ስብስብ አይደለንም” ያሉትም ሌላው ሀቅ ነው፡፡
በተደጋጋሚ የምናሰማው እሮሮ መጠነ ሰፊ ሆኗል፡፡ ሙስና አጠጠ፣ ት/ቤቶች ጥራት የላቸውም፡፡ መሠረተ - ጤና እንደምንፈልገው አልተስፋፋም፡፡ ተቋማት ይቋቋማሉ እንጂ አፈፃፀም የላቸውም፡፡ ባንኮች ንፅህናቸው አልተፈተሸም የከፍተኛ አመራሩ ችግር አለበት፡፡ ከፖለቲካ ልዩነት፤ ከሃይማኖት ልዩነት፣ ከዘር ልዩነት ነፃ ነን እንበል እንጂ ጣጣው አልለቀቀንም፡፡ “ሃጢያቱ ከተደጋጋመ ፅድቅ ይመስላል” ይሏልና፣ ቆም ብለን ተግባር ላይ እናተኩር!!




Saturday, 26 March 2016 11:01

የዘላለም ጥግ

(ስለ መምህራን)
• ግሩም መምህር ተስፋን ሊያነቃቃ፣ ፈጠራን
ሊያቀጣጥል፣ የመማር ፍቅርን ሊያሰርፅ
ይችላል፡፡
ብራድ ሄነሪ
• ጐበዝ አስተማሪ እንደ ጐበዝ አዝናኝ፣
በመጀመሪያ የአድማጮቹን ትኩረት መያዝ
አለበት፤ ከዚያ በኋላ ትምህርቱን ማስተማር
ይችላል፡፡
ጆን ሄንሪክ ክላርክ
• ትምህርት ለህይወት ስኬት ቁልፍ ነው፤
መምህራን በተማሪዎቻቸው ህይወት ውስጥ
ዘላቂ ተፅዕኖን ይፈጥራሉ፡፡
ሰሎሞን ኦርቲዝ
• የዘመናዊ መምህር ተግባር ደኖችን መቁረጥ
አይደለም፤ በረሃውን በመስኖ ማጥገብ እንጂ፡፡
ሲ. ኤስ. ሌዊስ
• ከመምህራን እገዛን ልታገኙ ትችላላችሁ፤ ነገር
ግን በራሳችሁ ብዙ መማር አለባችሁ፤ በባዶ
ክፍል ውስጥ ብቻችሁን በመቀመጥ፡፡
ዶ/ር ሴዩስ
• ጆሮ ከሰጣችሁት ሁሉም ሰው አስተማሪ ነው፡፡
ዶሪስ ሮበርትስ
• ግሩም መምህር ቁርጠኛ ሰው ነው፡፡
ጊልበርት ሂግሄት
• እንዴት ማሰብ እንዳለባቸው የሚያውቁ፣
አስተማሪ አያስፈልጋቸውም፡፡
ማሃትማ ጋንዲ
• ትክክለኞቹን መካሪዎችና መምህራን
በትክክለኛው ጊዜ በማግኘቴ ዕድለኛ ነበርኩ፡፡
ዴምስ ሌቪን
• የተዋወቅኋቸው፣ አብረውኝ የሰሩ ወይም
ታሪካቸውን ያነበብኩላቸው ሰዎች ሁሉ በአንድ
ወይም በሌላ መንገድ አስተማሪዎቹ ነበሩ፡፡
ሎሬታ ያንግ
• ስኬት ቀሽም አስተማሪ ነው፡፡ ብልህ ሰዎች
አንሸነፍም ብለው እንዲያስቡ ያማልላል፡፡
ቢል ጌትስ
• ልዩነት የሚፈጥረው መምህሩ እንጂ መማሪያ
ክፍሉ አይደለም፡፡
ማይክል ሞርፑርጐ