Administrator

Administrator

     ለዚህ ፅሁፍ መነሻ የሆነን ቅዳሜ ታህሳስ 23 ቀን 2008 ዓ.ም በአዲስ አድማስ የነፃ አስተያየት አምድ ላይ በእድገትና ትራንስፎርሜሽን ዕቅድ ዘመን በጥቃቅንና አነስተኛ ኢንተርፕራይዞች ልማት ከ10.6 ሚሊዮን በላይ የሥራ እድል ተፈጥሯል የሚለውን የመንግስትን ሪፖርት፣ ከእውነት የራቀ ነው በሚል ለንባብ የበቃው የአቶ ዮሐንስ ሰ. ፅሁፍ ነው፡፡
ፀሐፊው በገለፁት መልኩ ጉዳዩ “ለመሳቂያና ለመቀለጃ ተዘጋጅቶ የተቀመጠ” ሳይሆን የጥቃቅንና አነስተኛ የሥራ ዘርፎችን ባህሪያትና የሚያስገኙትን ጠቀሜታ አስመልክቶ የዳበረ ግንዛቤ ካልነበረበት፣ በዘርፉ ስራዎች ላይ ከተሰማራው አስፈጻሚ አንስቶ በህብረተሰቡ መካከል ሰፊ የአመለካከት ክፍተት በነገሰበት፣ ሥራውን በታሰበው ልክ ሊፈፅም የሚችል አደረጃጀትና ብቁ የሰው ሃይል ባልተሟላበት ሁኔታ እጅግ ፈታኝ ተግዳሮቶችን በማለፍ የተገኘ ውጤት ነው፡፡
አሁን ያለንበት ወቅት የምንቀልድበት ሳይሆን እያንዳንዷ የእለት ተእለት እርምጃችን በህዝባችን የኑሮ ደረጃ ለውጥና በሀገሪቱ ቀጣይ እጣ ፈንታ ላይ የከበረ ዋጋ እንዳላት በእጅጉ ተገንዝበን፣ ከድህነት ጋር የሞት ሽረት ትግል የምናካሂድበት ነው፡፡
አቶ ዮሐንስ ሰ. ይህን ፅሁፍ ለመፃፍ ሲያስቡ፣ ከማዕከላዊ ስታቲስቲክስ ባለስልጣን አገኘሁት ባሉት ቁንፅል መረጃ ላይ ብቻ ከመንጠልጠል ይልቅ የዘርፉን መረጃዎችንም ለማየት ቢሞክሩ፤ ከተቻለም ተፈጠረ የተባለው የሥራ እድል እንዴትና ለማን ተፈጠረ ብለው ሥራውን ወደሚመራው ተቋም ብቅ ቢሉ ኖሮ፣ የሥራ ዕድል ፈጠራችን  ያስገኘው ውጤት የብዙዎችን ህይወት የለወጠ፣ የብዙዎች የድካም ፍሬ እንጂ ፌዝ እንዳልሆነ በተጨባጭ ይረዱ ነበር፡፡
ይህም ካልሆነ ሩቅ ሳይሄዱ በአካባቢያቸው በሚገኘው የዘርፉ የአንድ ማዕከል አገልግሎት መስጫ ጣቢያዎች ጐራ ብለው ሥራ ፈላጊዎችን ለመለየት፣ ለማደራጀት፣ ሥራ ለማስጀመር፣ የገበያ ትስስር ለመፍጠርና መንግስታዊ ድጋፎችን ለማመቻቸት የተሰሩ ሥራዎችንና ያስገኙትን ውጤት በተጨባጭ አስተውለው ቢሆን ኖሮ ይህን የተዛባ ጽሑፍ ለመጻፍ ባልበቁ ነበር፡፡
በጥቃቅንና አነስተኛ ኢንተርፕራይዞች ልማት ዘርፍ በተለይም በስራ እድል ፈጠራው ባለፉት አመታት የተከናወነው ሥራ፣ በእርግጥም የተሳካ እንደነበር የፍሬወ ተቋዳሽ የሆኑ ዜጐች በተጨባጭ የሚመሰክሩትና እኛም በሙሉ መተማመን የምንናገረው፣ ከፌዴራል እስከ ክልል ያሉ አስፈጻሚ አካላት የአመታት ልፋትና ድካም ውጤት ነው፡፡ ከዘርፉ የአንደኛው የእድገትና ትራንስፎርሜሽን ዕቅድ አፈፃፀም ለማየት እንደሚቻለው፣ ለ3.2 ሚሊዮን ዜጐች የሥራ ዕድል ለመፍጠር ግብ ተጥሎ፣ በመደበኛው የኢንተርፕራይዞች ልማት ለ7,017,869 ዜጐች፣ በመንግስት ግዙፍ ፕሮጀክቶች ለ3,637,786 ዜጐች፣ በጠቅላላው ለ10,655,655 ዜጐች የሥራ ዕድል ተፈጥሯል፡፡
በተጠቀሰው የአምስት አመታት ጊዜ ውስጥ የተፈጠረውን የስራ እድል ዘርዘር አድርገን ስናየው፤ በቋሚነት 6‚029‚875 (56.6 ከመቶ)፣ በጊዜያዊነት 4‚625‚780 (43.4 ከመቶ) ሲሆን፣ በመደበኛው የኢንተርፕራይዞች ልማት ፕሮግራም ከተፈጠረው የስራ እድል በቋሚነት 4‚543‚240 (64.8 ከመቶ)፣ በጊዜያዊነት 2‚474‚629 (35.2 ከመቶ) እንዲሁም፣ በመንግስት ግዙፍ ፕሮጀክቶች በቋሚነት 1‚486‚635 (40.8 ከመቶ)፣ በጊዜያዊነት 2,151‚151 (59.2 ከመቶ) ነው፡፡
በአጠቃላይ ከተፈጠረው የስራ እድል ውስጥ ተጠቃሚ የሆኑ ሴቶች 4‚387‚701 (41.2 ከመቶ) ሲሆኑ ባለፉት አምስት አመታት ውስጥ በዘርፉ ልማት 766‚990 ኢንተርፕራይዞችን ለማፍራትም ተችሏል፡፡ በእነዚህ ኢንተርፕራይዞች አማካኝነት በሚሊዮን የሚቆጠሩ ዜጐችን ተጠቃሚ ያደረገ ቋሚና እንደ ስራው ባህሪ የቅጥር ጊዜው ተለዋዋጭ የሆነ ጊዜያዊ የሥራ ዕድል ተፈጥሯል፡፡
የማእከላዊ ስታቲስቲክስ ኤጀንሲ፤የከተማ ነዋሪዎችን ቁጥር አስመልክቶ ያወጣውን መረጃ ከላይ ከቀረቡት የዘርፉ መረጃዎች ጋር በማነጻጸር የቀረበው የአቶ ዮሐንስ ጽሑፍ፣ ስህተት አንድ ብሎ የጀመረው በዚህ መልኩ የሥራ ዕድል የተፈጠረላቸውን ዜጐች ማንነት በጥልቀት መቃኘት ካለመቻል የተነሳ ነው፡፡ ከላይ እንደተገለፀው በጥቃቅንና አነስተኛ ኢንተርፕራይዞች ልማት፣ የሥራ ዕድል የተፈጠረው በሁለት መልኩ ነው፡፡ አንደኛው በዘርፉ መደበኛ የኢንተርፕራይዞች ልማት ፕሮግራም በምንለው ሥር ባሉ የስራ ዘርፎች ማለትም በማኑፋክቸሪንግ፣ በኮንስትራክሽን፣ በንግድ፣ በአገልግሎትና በከተማ ግብርና ንዑስ ዘርፎች ሲሆን ሁለተኛው ደግሞ መንግስት በተለያዩ የሀገሪቱ ክፍሎች በሚያከናውናቸው ግዙፍ የልማት ፕሮጀክቶች ነው፡፡ ጸሐፊው ከመሰረቱ የሳቱት ጉዳይ በእነዚህ ዘርፎች የሚሰማሩ ሥራ ፈላጊ ዜጐች፣ የግድ በከተማ ነዋሪነት ብቻ የተመዘገቡ ናቸው ብለው መነሳታቸው ላይ ነው፡፡
የዘርፉን ስትራቴጂ ተግባራዊ ለማድረግ ከተዘጋጁ መመሪያዎች መካከል አንዱ በሆነው የአንድ ማዕከል አገልግሎት አሰጣጥ መመሪያ ላይ በግልጽ እንደተቀመጠው፣ በከተማ በሚፈጠሩ የስራ ዕድሎች ውስጥ ተሳታፊ ለመሆን የሚፈልግ ማንኛውም ዜጋ፣ ከሚኖርበት የገጠር ቀበሌ ሥራ ፈላጊነቱን የሚያረጋግጥ ማስረጃ በማቅረብ፣ በሚኖርበት ወረዳ ውስጥ በሚገኝ የአንድ ማዕከል አገልግሎት መስጫ ጣቢያ በስራ ፈላጊነት ሊመዘገብ ብሎም ከሚፈጠሩት የሥራ እድሎች ተጠቃሚ ሊሆን ይችላል፡፡ በአጭሩ፣ባለፉት ዓመታት በተፈጠረው የሥራ ዕድል ተጠቃሚ የሆኑ ዜጎች በከተማዋ ነዋሪነት የተመዘገቡ ብቻ ናቸው ማለት አይደለም፡፡
በመደበኛው የኢንተርፕራይዞች ልማት ፕሮግራም የሥራ ዘርፎች ከተፈጠረው የሥራ ዕድል በተጨማሪ የመንግሥት ግዙፍ ፕሮጀክቶች በምንላቸው የስኳር ፋብሪካ፣ የህዳሴ ግድብ፣ የማዳበሪያ ፋብሪካ፣ የባቡርና የገጠር መንገድ ግንባታ፣ የኤሌክትሪክና የቴሌኮሙኒኬሽን ስራዎች፣ የቤቶች ልማትና የከተማ ማስዋብ፣ የኮብል ስቶን፣ የውስጥ ለውስጥ መንገዶች ግንባታን ጨምሮ በተለያዩ ፕሮጀክቶች ላይ የሥራ ዕድል የተፈጠረላቸው ዜጎች በርካታ መሆናቸውን በተጨባጭ ማስተዋል ይቻላል፡፡ እዚህ ላይ ልብ ልንል የሚገባን ባለፉት ዓመታት የተፈጠረው የሥራ ዕድል ከመደበኛው የኢንተርፕራይዞች ልማት ፕሮግራም በተጨማሪ በእነዚህ ፕሮጀክቶች ውስጥ በሚሰሩ ኢንተርፕራይዞች አማካኝነትና በግለሰብ ደረጃ በቋሚነትና  በጊዜያዊነት፣ በየጊዜው ለአጭር ጊዜ ሊሆን ይችላል /ከ1 ዓመት ያልበለጠ/ ወደ ሥራ የገቡ ዜጎችንም ጭምር የሚያካትት ነው፡፡
ይህን ሁኔታ ከግምት በማስገባት፣ የመንግስት ግዙፍ ፕሮጀክቶች በሚገኙባቸው አካባቢዎች፣ ሥራ ፈላጊ ዜጎች የሚመዘገቡበትና ወደ ሥራ እንዲገቡ ሁኔታዎች የሚመቻችበት የአንድ ማዕከል አገልግሎት መስጫ ጣቢያዎችን ማቋቋም እንደሚያስፈልግ ከግንዛቤ በመግባቱ፣ በተለያዩ የመንግስት ፕሮጀክቶች ላይ ጣቢያው ተቋቁሟል፡፡ ጸሐፊው ሩቅ ሳይሄዱ በአዲስ አበባ በቤት ልማት ፕሮጀክቶችና የኮብልስቶን መንገድ ሥራዎች ላይ በቋሚና በጊዜያዊነት የተሰማሩ ነገር ግን የአዲስ አበባ ከተማ የነዋሪነት መታወቂያ ያልያዙ ዜጎችን እጅግ ከፍተኛ በሚባል መጠን ማግኘት የሚችሉ ሲሆን በየክልሉ በሚካሄዱ ፕሮጀክቶች የሚሰሩ ዜጎች የየአካባቢው የገጠር ቀበሌ ነዋሪ ወጣቶችንም ጨምሮ እንጂ የከተማ ነዋሪዎች ብቻ አለመሆናቸውን በቀላሉ ማረጋገጥ የሚችሉት ነው፡፡
ምንም እንኳን የዘርፉ የሥራ እድሎች የሚፈጠሩት በከተማ ውስጥ እንደሆነ በስትራቴጂው ላይ ቢገለፅም ባለፉት ዓመታት የአርሶ አደሩ የአኗኗር ሥርዓት ላይ የመጣውን ለውጥ ተከትሎ በገጠር ቀበሌዎች እንደ ንግድ፣ አገልግሎትና የከተማ ግብርና የመሳሰሉ የሥራ እድሎችን ለመፍጠር የሚያስችል ምቹ ሁኔታ እንዳለ ተስተውሏል፡፡ በዚህም መሰረት በኦሮሚያና በአማራ ክልሎች ከ2007 ዓ.ም ጀምሮ በጥቃቅንና አነስተኛ ኢንተርፕራይዞች ልማት ዘርፍ፣ “የገጠር የሥራ ዕድል ፈጠራ” በሚል ራሱን ችሎ በተከናወነ ፕሮጀክት ለበርካታ ዜጎች የሥራ ዕድል ለመፍጠር ተችሏል፡፡ እነዚህ ዜጎች በከተማ ነዋሪነት የተመዘገቡ ባይሆኑም ከሀገሪቱ ሀብት በፍትሃዊነት የመካፈል መብት ያላቸው ኢትዮጵያውያን እንጂ ጸሀፊው እንደሚሉን ከቅርብ የጎረቤት ሀገራት አልያም ከባህር ማዶ የመጡ ባዕዳን አይደሉም፡፡
በዘርፉ የሥራ ዕድል የተፈጠረላቸው ነገር ግን የግድ የከተማ ነዋሪ መሆን ከማይጠበቅባቸው ዜጎች መካከል ከተለያዩ የቴክኒክና ሙያ እንዲሁም ከፍተኛ የትምህርት ተቋማት የሚወጡ ዜጎችን መጥቀስ ይቻላል፡፡ ከ2004 ዓ.ም ጀምሮ መንግስት ለምሩቃን የሥራ ዕድል ፈጠራ በሰጠው ትኩረት፣ እስከ ሰኔ 2007 ዓ.ም ድረስ ለ407, 682 ምሩቃን የሥራ ዕድል ተፈጥሯል፡፡ ምሩቃንን ወደ ሥራ ለማስገባት በተዘጋጀው መምሪያ ላይም ማንኛውም ምሩቅ በሚፈልገው የሥራ ዘርፍ፣ በመረጠው የሀገሪቱ ክፍል ከትውልድ ሥፍራው ከዚህ በፊት በዘርፉ ተደራጅቶ እየሰራ አለመሆኑን የሚያሳይ ማስረጃ በማቅረብ፣ የዘርፉ የሥራ ዕድል ፈጠራ ተጠቃሚ መሆን ይችላል፡፡
የሥራ ፈጠራችን ዋነኛ ግብም ለኢንዱስትሪ ሽግግሩ መሰረት የሚሆኑ ኢንተርፕራይዞችን በስፋት ከማፍራት በተጨማሪ አቅም በፈቀደ መጠን በመደበኛም ሆነ መደበኛ ባልሆኑ የመንግስት የልማት ፕሮጀክቶች፣ በቋሚነት ይሁን በጊዜያዊነት፣ የከተማ ነዋሪዎችም ሆኑ በሚፈጠሩ የሥራ ዕድሎች ተጠቃሚ ለመሆን የሚሹ ማናቸውም ዜጎች፣ ሰርተው ራሳቸውንና ሀገራቸውን ሊለውጡ የሚችሉበትን ሁኔታ ማመቻቸት ነው፡፡ ይህንን መሰረት በማድረግም ባለፉት አመታት በዘርፉ ልማት ያከናወናቸው ሥራዎች ወደ ሥራ መግባት ከሚገባቸው ዜጎቻችን አንጻር ስንመዝነው በቂ ነው ማለት ባይቻለንም፣ ጸሐፊው እንዳጣጣሉት ከእውነት የራቀና የማይጨበጥ ሳይሆን የበርካቶችን ህይወት የለወጠና በየአካባቢያችን የምናየው ሀቅ ነው፡፡
በመሆኑም አቶ ዮሐንስ፤ እንደ ዜጋ በሀገራቸው የልማት ሥራዎች ላይ ግልጽ ያልሆኑላቸውን ነገሮ የመጠየቅ መብታቸውን የምናከብር በመሆኑና በጽሁፋቸው ያሰፈሩት ጉዳይም ምን አልባትም በቂ መረጃ ካለመያዝ የመነጨ ይሆናል ብለን ስለምንገምት፣ወደፊት ተጨማሪ ማብራሪያ የሚሹ ከሆነ በራችን ሁሌም ክፍት መሆኑን በዚሁ አጋጣሚ ለመግለጽ እንወዳለን፡፡
የፌደራል የጥቃቅንና አነስተኛ ኢንተርፕራይዞች ልማት ኤጀንሲ
የሕዝብ ግንኙነትና ኮሙኒኬሽን ዳይሬክቶሬት

     ከዕለታት አንድ ቀን አንድ እጅግ ጉረኛ ሰው በአንድ መንደር ከሚስቱ ጋር ይኖር ነበረ፡፡ በድፍረት የማይከራከርበት ጉዳይ የለም፡፡ የሱን አሸናፊነት አጉልቶ ሌሎች ወንዶችን አኮስሶ ከማውራት ቦዝኖ አያውቅም፡፡
“ዛሬ አንዱን አንድ ቡና ቤት አግኝቼ ሳይቸግረው ለከፈኝ” ይላታል ለሚስቱ፡፡
ሚስትም፤
“በምን ጉዳይ ለከፈህ?” ትለዋለች፡፡
ባል፤
“እንደው ቢፈርድበት ነው እንጂ ነገሩ የሚያጣላ ሆኖ መሰለሽ? “አጐቴ በጣም አጭር ድንክዬ ሰው ነው፡፡ እኔ ደግሞ ከጥንቱም ድንክ ሰው እጣ - ክፍሌ አይደለም” አይልልሽም?”
ሚስት፤
“በጄ፡፡ ከዛስ ምን ሆነ?”
ባል፤
“ሾርኔ ንግግሩ ገብቶናል፡፡ ወንድ ልጅ ግን በአግቦ ሳይሆን በቀጥታ ነው መናገር ያለበት” አልኩኝ፡፡
ሚስት፤
“ለምን እንደዛ አልከው፤ እሱ የሚያወራው’ኮ ስለአጐቱ ነው?”
ባል፤
“አንቺ የዋህ ነሽ፡፡ እኔ አጭር መሆኔን ስላየ’ኮ ነው በጐን ወጋ ሊያደርገኝ የሞከረው፡፡”
ሚስት፤
“ከዛስ ምን ሆነ?”
ባል፤
“ጊዜ የሰጠሁት መሰለሽ፤ እንደ ነብር ተወርውሬ በቡጢ ማንጋጭልያውን አወለቅሁለታ!”
ሚስት፤
“አንተ ሰውዬ ይሄ ግሥላነት አያዋጣህም፡፡ ባለፈው ሣምንት እንኳን ከሶስት ሰው ጋር ተጣላሁ ብለኸኝ ነበር፡፡ ትዕግሥት ቢኖርህ ይሻላል” አለችው፡፡
ባል፤
“እኔኮ ካልነኩኝ አልነካም” ይላታል፡፡
አንድ ቀን ማታ ባል በጣም አምሽቶ ደም በደም ሆኖ ይመጣል፡፡ ሚስት ደንግጣ ከበር ትቀበለዋለች፡፡
“ምነው ምን ሆንክ አካሌ?”
ባል፤
“ካንድ መናጢ ጋር ተደባድቤ ድንገት ቀደመኝ”
ሚስት፤
“እንዴ፤ አላስተረፈህም’ኮ! ጭንቅላትህ ደግሞ ተፈነካክቷል፡፡ ሰውዬው ዱላ ይዞ ነበር እንዴ?”
ባል፤
“ኧረዲያ፤ ደሞ ዱላ የመያዝን ያህል ወንድነት ከየት አባቱ አምጥቶ ነው! የኔኑ ነጥቆ ነው እንጂ!”
*    *    *
ያልሆነውን ነን፣ ያላደረግነውን አድርገናል ብሎ ጉራ መንዛት መጨረሻው አሰቃቂ ነው፡፡ ከቶውንም ጥቃቅን የሚመስሉ ግን በአጉሊ መነፅር ስናያቸው አገራዊ ፋይዳ ያላቸው አያሌ ነገሮች አሉ፡፡ የምንዋሸውም ሆነ ጉራ የምንነዛው ቅርባችን ላለ ሰው መሆኑ አስገራሚ ነው፡፡ ምክንያቱም ብዙም ውሎ ሳያድር መጋለጡ በጣም ግልጽና አይቀሬ በመሆኑ ነው፡፡ ዋሽተን የተናገርነውን ማጠፍ ሲያቅተን፣ በጉልበት ለማሳመን መሞከር ይመጣል፡፡ ያኔ መሠረታዊ ሰብዓዊ መብትንም ሆነ ዲሞክራሲያዊ መብትን መጣስ ይመጣል፡፡ ፍትሕን እኔን በሚያግዝ መልኩ ካላስቀመጣችሁ ማለት ይመጣል፡፡ እኔ ላልኩት ካላጨበጨባችሁ ሁላችሁም ልክ ያልሆናችሁት ነገር አለ፤ ማለት ይከተላል፡፡ ግልጽነትንና ተጠያቂነትን የበላ ጅብ አልጮህ ይላል፡፡ የህዝብን ዕውነተኛ ችግር እንዳይገለጽ መጫን ይበራከታል፡፡ አመለካከትን በነፃነት መግለጫ መድረክ ይጨልምና ሆድ ለሆድ መነጋገር ዓይነተኛ ዘዴ እየመሰለ ይመጣል፡፡ መገናኛ ብዙሃን የህዝብ ድምጽ ማሰሚያ መሆናቸው ይቀራል፡፡ ከዚህ ዲበ - ኩሉ ይሰውረን!
ለአንድ አገር ህዝባዊ ውይይት መኖር አስፈላጊ ነው፡፡ ችግሮች ከአዕምሮ አዕምሮ ይዘዋወራሉ፡፡ ብሶቶች ይብላላሉ፡፡ የታፈኑ ሃሳቦች ይፍታታሉ፡፡ “አካፋን አካፋ” የማለት ባህል ይዳብራል፡፡ ሌባውን ከጨዋው የመለየት ዕድል ይሰፋል፡፡ ህዝብ ዕውነቱን የመናገር አጋጣሚ ሲያገኝ ሹማምንትን የማረም፣ የመተቸት፣ የመገሰፅ፣ አስፈላጊ ሆኖ ሲገኝ ከመንበራቸው የማውረድ ሁኔታዎች ይፈጠራሉ፡፡ “ዳቦ ራበን” ብሎ ለሚጮህ ህዝብ፤ “ለምን ኬክ አይበሉም?” ብላ እንደመለሰችው እንደ ንግሥት ሜሪ አንቷኔት ያለ ቅንጡ አመራር አይኖርም፡፡ “ህዝባዊ ሸንጐ የአፍ መፍቻ ቋንቋ ነው” ይላሉ ፈላስፋ ፀሐፍት፡፡ ህዝባዊ ውይይትን አቅጣጫ በማስያዝ ሰበብ ጮሌ ሊጠቀምበት እንደሚችል ግን ልብ ብሎ ማየት ያስፈልጋል፡፡ ማንም ይሁን ማን የህዝብን ትኩረት በመሳብ ወደግል ጥቅሙ ልጐትት ሲል ገመዱን ለመበጠስ ዝግጁ መሆን ብልህነትም፣ ኃላፊነትም ነው፡፡ የመልካም አስተዳደር የንቅናቄ መድረክ፣ በተለይ ምዝበራን ከማጋለጥ አንፃር በየቦታው እየተሞከረ ያለው ሂደት፣ የሀገርን ሀብትና በሺዎች የሚቆጠሩ ሄክታሮችን ያድናል፡፡
የዳነውን ሌሎች እንዳይመዘብሩት የሚቆጣጠሩ ጠንቃቃ አካላት ያስፈልጋሉ፡፡ ነገሮች እንዳይድበሰበሱ፣ ጥያቄዎች በተጠየቁበት ገጽ እንዲመለሱ ማድረግ ያስፈልጋል፡፡ የተጠየቁትን ትተው ያልተጠየቁትን የሚመልሱ ተጋላጫ አመራሮችን ለነገሮች ልጓም አበጅቶ ፈራቸውን እንዳይለቁና በትክክል ወንጀላቸው እንዲለይ ማድረግ ያስፈልጋል፡፡ አለበለዛ በለመደ ምላሳቸው ወንጀሉን ለቀና ተግባር እንዳደረጉት ሊያስመስሉት ይችላሉ፡፡ ስለሆነም “ከዝሆንና ከአንበሳ ማን ይበልጣል” ቢለው፤ “ከሁሉም ከሁሉም አሣ ሙልጭልጭ ነው” አለው፤ እንደተባለው እንዳይሆን መጣር የአባት ነው!

    በህትመት፣ ወረቀትና እሽግ ሥራዎች ላይ ያተኮረና ከ40 በላይ የአገር ውስጥና የውጭ ድርጅቶች የተሳተፉበት አለምአቀፍ ኤክስፖ ትላንት በሚሊኒየም አዳራሽ ተከፈተ፡፡
በፕራና ፕሮሞሽን ተዘጋጅቶ ከጥር 13-15 በሚቆየውና በኢንዱስትሪ ሚኒስቴር ሚኒስትር ዴኤታ በዶ/ር መብራቱ መለስ በተከፈተው በዚሁ “አፍሪ ፕሪንት ኤንድ ፓኬጂንግ ኤክስፓ” ላይ፤ አታሚዎች፣ የህትመት መሣሪያ አስመጪዎች፣ የህትመት ማስታወቂያ ድርጅቶች፣  የወረቀት አምራቾችና አስመጪዎች፣ የግራፊክ ዲዛይን ድርጅቶች እንዲሁም ከወረቀት ጋር የተያያዙ ሥራዎችን የሚሰሩ የአገር ውስጥና የውጭ ድርጅቶች ተሣታፊ ሆነዋል፡፡
በኤክስፖው በዘርፉ የተሰማሩ ድርጅቶች የንግድ ትስስር እንዲፈጥሩና የቴክኖሎጂና የዕውቀት ሽግግር እንዲያደርጉ ታስቦ መዘጋጀቱን የተናገሩት የፕራና ፕሮሞሽን ዋና ሥራ አስኪያጅ አቶ ነቢዩ ለማ፤ ፕሮግራሙ በአገራችን በዘርፉ ለተሰማሩ ድርጅቶ ከፍተኛ አስተዋፅኦ ያደርጋል የሚል እምነት አለኝ ብለዋል፡፡ በዚህ ኤክስፖ ላይ ለመሳተፍ ከአሜሪካ፣ ከአውሮፓና ከኤዥያ የመጡ ባለሀብቶችና የድርጅቶች ተወካዮች መኖራቸውንም አቶ ነቢዩ ተናግረዋል፡፡

ሮተሪ ክለብ በአዲስ አበባ የተቋቋመበትን የ25ኛ ዓመት በዓል ዛሬ ያከብራል፡፡ በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ የጥናትና ምርምር ማዕከል በሚከበረው በዚሁ በዓል ላይ የክለቡ አባላት፣ በጐ ፈቃደኞችና ታዋቂ ሰዎች ይገኙበታል ተብሏል፡፡
እ.ኤ.አ ፌቡራሪ 23 ቀን 1905 ዓ.ም በቺካጐ የተቋቋመው ሮተሪ ክለብ፤ በአሁኑ ወቅት በ200 አገራት ውስጥ የሚገኙ 33 ሺ ክለቦችንና ከ1.2 ሚሊዮን በላይ አባላትን ይዟል፡፡
ክለቡ በበጐ ፈቃደኛ አባላቱ አማካኝነት በመሠረታዊ ትምህርት አቅርቦት፣ በእናቶችና ሕፃናት ጤና፣ በበሽታ መከላከል፣ በንፁህ የመጠጥ ውሃና በንፅህና አጠባበቅ እንዲሁም በማህበረሰብ ኢኮኖሚ ልማት ላይ እየሰራ ይገኛል፡፡

Saturday, 16 January 2016 10:39

የኪነት ጥግ

(ስለ ሥነጥበብ)
• ሁሉም ሰዓሊ መጀመሪያ አማተር ነበር፡፡
ራልፍ ዋልዶ ኢመርሰን
• ስዕል ቃላት አልባ ግጥም ነው፡፡
ሆራስ
• ስዕል ውብ መሆን የለበትም፡፡ ትርጉም
ያለው መሆን ነው ያለበት፡፡
ዱዋኔ ሃንስ
• ስዕል ለመሳል ዓይናችሁን ጨፍናችሁ
መዝፈን አለባችሁ፡፡
ፓብሎ ፒካሶ
• ጥበብ ድንቁርና የሚባል ጠላት አላት፡፡
ቤን ጆንሰን
• ጥበብ የሰው ተፈጥሮ ነው፡፡ ተፈጥሮ
የእግዚአብሔር ጥበብ ነው፡፡
ጄምስ ቤይሌይ
• የጥበብ ተልዕኮ ተፈጥሮን መወከል እንጂ
መኮረጅ አይደለም፡፡
ዊሊያም ሞሪስ ሃንት
• ጥበብ የነፃነት ልጅ ናት፡፡
ፍሬድሪክ ሺለር
• ጥበብ ቤትን ሳይለቁ የማምለጪያ ብቸኛ
መንገድ ነው፡፡
ትዊላ ዛርፕ
• ስዕል ሃሳቦቼን የማስርበት ምስማር ነው፡፡
ጆርጅስ ብራኪው
• ሰዓሊ የሚከፈለው ለጉልበቱ አይደለም፤
ለርዕዩ እንጂ፡፡
ጄምስ ዊስትለር
• የሰዓሊ ዋና ሥራው ወደ ሰው ልጅ ልቦና
ብርሃን መላክ ነው፡፡
ጆርጅ ሳንድ
• ዓይኖቼ የተፈጠሩት አስቀያሚውን ነገር
ሁሉ ለመሰረዝ ነበር፡፡
ራኦል ዱቲ
• ሰው በእርሳስ መሳል ሲያቅተው በዓይኑ
መሳል አለበት፡፡
ባልዙስ

    ታዋቂው ገጣሚና ደራሲ በዕውቀቱ ስዩም “ከአሜን ባሻገር” የተሰኘ አዲስ መጽሃፍ ያሳተመ ሲሆን በመጪው ሳምንት ገበያ ላይ ይውላል ተብሏል፡፡ “በመጽሐፌ ከጉዞ፣ ከኑሮና ከምርምር የቀሰመኩትን እውነታ ለማካፈል ጥረት አድርጌያለሁ፡ ፡” ብሏል፤ በዕውቀቱ በፌስቡኩ ላይ ባሰፈረው ጽሁፍ፡፡በ2004 ዓ.ም በለንደን ኦሎምፒክ ከዓለም ዕውቅ ገጣሚያን ጋር የግጥም ሥራውን ያቀረበው በዕውቀቱ፤በአሁኑ ወቅት በአሜሪካ ሃዋርድ ዩኒቨርሲቲ በትምህርትና ምርምር ላይ ይገኛል፡፡
ከዚህ ቀደም ደራሲው “ነዋሪ አልባ ጎጆዎች”፣ “በራሪ ቅጠሎች;፣ “እንቅልፍና ዕድሜ”፣ “መግባትና መውጣት” የተሰኙ የሥነጽሁፍ ሥራዎቹን ለንባብ አብቅቷል፡፡

  ባለፈው ሐምሌ፣ ለሁለተኛ ጊዜ ከወህኒ ያመለጠው፤ በ10 ሜትር ጥልቀት 1500 ሜትር መተላለፊያ ዋሻ                አስቆፍሮ ነው።
              ሰሞኑን፣ በልዩ ሃይል የተወረረው መኖሪያ ቤቱም፣ የማምለጫ ዋሻ ተሰርቶለታል - ጀርመን ልኮ                ባሰለጠናቸው መሃኒዲሶች።  
             በሜክሲኮ፣ የአደንዛዥ እፅ አስተላላፊዎች፣ በገንዘብና በትጥቅ የፈረጠሙ ቡድኖች ናቸው - 100                ከንቲባዎችን ገድለዋል።
    ከኮሎምቢያ ወደ አሜሪካ በሚያመራው፣ የአደንዛዥ እፅ ማስተላለፊያ መስመር መሃል ላይ ያለችው ሜክሲኮ፣ ከአሰቃቂ የግድያ ዜናዎች እፎይ ያለችበት ጊዜ የለም። የዘወትር ሕይወት ነው። ከሳምንት በፊት የተካሄደ የቀብር ስነስርዓትም፣ በሜክሲኮ ምድር፣ እንግዳ ነገር አልነበረም። ሟቿ፣ ጌሲላ ማዎቴ፣ አደንዛዥ እፅ በሚያስተላልፉ ታጣቂዎች ነው የተገደለችው። ለዚያውም፣ በከተማ የከንቲባ ምርጫ ያሸነፈቸው ጌሲላ፣ ደስታዋን የማጣጣም ጊዜ አልነበራትም። ስልጣን በተረከበችበት እለት ተገድላለች ይላል የታይም መፅሄት የሰሞኑ እትም። ካሁን በፊትም፣ 100 ከንቲባዎች በአደንዛዥ እፅ አስተላላፊ ቡድኖች እንደተገደሉ መፅሄቱ ገልጿል።
ታዲያ፣ ‘የአደንዛዥ እፅ አስተላላፊ’ ሲባል፣... ‘አይነት’ አለው። የየመንደሩ ዋና አለቆች፣ ታጣቂዎችን በቡድን አደራጅተው ያሰራሉ። የየከተማው አውራዎችም አሉ - የበላይነት ለማግኘትና ሙሉ ለሙሉ ለመቆጣጠር፣ ዘወትር ይገዳደላሉ፤ ይጨፋጨፋሉ። እነዚህን ሁሉ ጠቅልለው፣ በየክልሉ የገነኑ መሪዎች ግን፣ ሚሊዮነሮች ከመሆናቸውም በላይ፣ እልፍ ታጣቂዎች እንደሚያዘምት ሃያል ገዢ ነው የሚታዩት። ግን፣ የያዝኩትን ይዤ ልኑር ብሎ ነገር የለም። የገናናዎቹ ሁሉ ቁንጮ ለመሆንና ገዢነታቸውን ለማስፋፋት፣ ፋታ በማይሰጥ ጦርነት ይጠመዳሉ። መንግስት ያለበት አገር አይመስልም። እናም፣ አንደኛው ወገን በጦርነቱ ከቀናው፣ ገናና የአደንዛዥ እፅ ጌታ ወይም ንጉሥ ይሆናል።
ከ1995 ዓ.ም ወዲህ፣ ዙፋኑን ተቆጣጥሮ የቆየው፣ የሜክሲኮ የአደንዛዥ እፅ ንጉሥ፣ ጆአኪን ጉስማን ይባላል። በቅፅል ስሙ፣ ኢል ቻፖ ይሉታል (አጭሬው እንደማለት ነው)። ከኢል ቻፖ በፊት፣ ስመ ገናና የአደንዛዥ እፅ ንጉሦች አልነበሩም ማለት አይደለም። ፓብሎ ኢስኮባርን መጥቀስ ይቻላል። የኢል ቻፖ ንግሥና ግን ለየት እንደሚል የዘገበው ፎርብስ፣ እስከ አሜሪካ ከተሞች ድረስ መረቡን ዘርግቶ፣ የማከፋፈያና የችርቻሮ አውታሮችን በማደራጀት፣ በታሪክ አቻ ያልተገኘለት የአደንዛዥ እፅ ሽያጭ እንዳካሄደ ገልጿል።
በሜክሲኮ ምድር፣ ከአገሪቱ ፕሬዚዳንት በመቀጠል፣ በሃያልነት የሚጠቀስ ‘ገዢ’ ኢል ቻፖ ነው። ገናናነቱ ግን፣ በሜክሲኮና በጎረቤት አገራት ብቻ አይደለም። በመላው አለም፣ ኢል ቻፖን የሚስተካከል የአደንዛዥ እፅ ወንጀለኛ የለም ብሏል ፎርብስ። ለዚህ የበቃውም፣ በአይምሬነቱና በጭካኔው ነው። ተቃናቃኞችን ማስገደል፣ መጨፍጨፍና ማጥፋት... ይሄ የተለመደ ነው። ሌላው ቀርቶ፣ ጥቂት ደቂቃ ያረፈደ የአደንዛዥ እፅ አመላላሽና አከፋፋይ እንኳ፣ በሕይወት እንደፈረደ ነው የሚቆጠረው - በኢል ቻፖ ግዛት።
እንዲህ፣ በጭካኔው፣ ከመንደርና ከከተማ አለቃነት፣ ወደ ላይ ብቅ ብቅ ማለት ሲጀምር ነበር፣ በ1985 ዓም ለመጀመሪያ ጊዜ የታሰረው። እንደ ወንጀሉ ብዛት ባይሆንም፣ የሃያ ዓመት እስር ተፈረደበት። ግን የእስር ቅጣቱን ሳያጠናቅቅ፣ በ1993 ዓ.ም ከወህኒ አመለጠ። የቆሸሹ ልብሶችን ወደ እጥበት የሚወስድ መኪና ውስጥ ተደብቆ ያመለጠው ኢል ቻፖ፣ እቅዱን ለማሳካት ለበርካታ የወህኒ ቤቱ ፖሊሶች ደሞዝ በመክፈል እንዲተባበሩት ማድረጉን ዩኒቨርሳል የተሰኘው ጋዜጣ ዘግቧል። የሜክሲኮ ፖሊሶች፣ ኢል ቻፖን ለመያዝ የከፈቱት የምርመራና የአደን መዝገብ፣ በአጭር ጊዜ አልተቋጨም። አስተማማኝ መረጃ ያገኙት፣ ከበርካታ ዓመታት በኋላ ነው - የዛሬ ሁለት ዓመት ገደማ። ከአራት በላይ ሚስቶች እንዳሉት የሚነገርለት ኢል ቻፖ፣ ወደ አንዲት የቀድሞ ሚስቱ መኖሪያ ቤት ጎራ ያለው፣ ደርሶ ለመመለስ ብቻ ሳይሆን፣ በዚያውም ከልጆቹ ጋር ለመሰንበት ነው።
መረጃው ትክክል ከሆነ፣ ኢል ቻፖን ለመያዝ አይከብደንም በሚል የተሰማሩት ፖሊሶች፣ እንደገመቱት አልሆነላቸውም። የቤቱን በር ገንጥለው ለመግባት ሞከሩ። በሩ፣ ግን ንቅንቅ አላለም። አያስታውቅም እንጂ፣ በጠንካራ ብረት ተደራርቦ ስለተሰራ፣ እንደ ካዝና በር፣ አይነኬ ሆነባቸው። በዚህም በዚያም ብለው፣ በስንት መከራ መግባታቸው ግን አልቀረም። አዩ፣ በረበሩ፣ ፈተሹ። ሰውዬው የለም። ለካ፤ መሬት ስር፣ አምስት ቤቶችን አቆራርጦ የሚያስወጣ፣ መተላለፊያ ዋሻ አሰርቶ ኖሯል። ፖሊሶቹ፣ ‘አመለጠ’ ብለው አልተቀመጡም። ሰውዬውም፣ ርቆ አልሄደም። ‘ሪዞርት’ ሆቴል ውስጥ፣ መሰንበቻውን ክፍሎች ተከራይቶ ተቀምጧል - ከሚስቱና ከሁለት ልጆቹ ጋር። 60 የባህር ሃይል ኮማንዶዎች፣ አካባቢውን በመቆጣጠር፣ ኢል ቻፖን አስረው ወደ ወህኒ መለሱት።
ኢል ቻፖ፣ እንደገና ከእስር ለማምለጥ፣ በርካታ አመታትን አልፈጀበትም። ከታሰረበት ክፍል ስር፣ በምድር ስር፣ ረዥም መተላለፊያ ዋሻ በማስቆፈር፣ አምና በ2007 ዓ.ም፣ አመለጠ። ከእስር ቤቱ ግቢ አልፎ፣ አንዲት አነስተኛ ቤት ድረስ፣ ከሰው እይታ ውጪ፣ በአስር ሜትር ጥልቀት የተቆፈረው መተላለፊያ ዋሻ፣ 1500 ሜትር ርዝመት አለው። የአየር ማስገቢ ቱቦና የመብራት መስመር ሁሉ ተዘርግቶለታል። በዚያ ላይ፤ አፈሩን በቁፋሮ ለማውጣትና በመጨረሻም ኢል ቻፖን ለማጓጓዝ፣ የሃዲድ መስመርና፣ በሃዲዱ ላይ የሚሄድ ሞተር ሳይክል... ምናለፋችሁ፤ ነገሩ ብዙ ተለፍቶበታል። ኢል ቻፖ፣ ከወህኒ ካመለጠ በኋላ፣ ለሆሊውድ አክተር ሾን ፔን በድብቅ ቃለምልልስ ሲሰጥ፣ ስለ ዋሻው አሰራር ተናግሯል። መተላለፊያ ዋሻውን የሰሩልኝ፣ የጀርመን ልኬ ያሰለጠንኳቸው መሃንዲሶች ናቸው ብሏል - አጅሬው።
አስገራሚው ነገር፣ ኢል ቻፖ፣ ለጋዜጠኛ ሳይሆን፣ ለሆሊውድ አክተር ለሾን ፔን፣ ቃለምልልስ የሰጠው፣ ከቃለምልልሱ ውጭ ሌላ ህልም ስለነበረው ነው። በሕይወቱ ዙሪያ፣ ፊልም የመስራት ህልም ነበረው ብሏል - የሳምንቱ አዲስ የኢኮኖሚስት መፅሄት እትም። ከፊልም ባለሙያዎችና ከተዋናዮች ጋር ለመነጋገር ሲሞክር ከርሟል። የሜክሲኮ ልዩ ሃይል፣ ኢል ቻፖን ለመያዝ አስተማማኝ መረጃ ያገኘውም በዚሁ አጋጣሚ ነው።
እንደተለመደው፣ ለአዳር የመረው መኖሪያ ቤት፣ ከመሬት ስር፣ ማምለጫ ዋሻዎች የተዘረጉለት ነው። ደግሞም፣ አምልጧል። ቱቦ ለቱቦ እየተሽለኮለከ፣ በጣም ርቆ ከሄደ በኋላ፣ ከዚያም ከቱቦው ወጥቶ የከተማ ዳርቻ ለመድረስ ሲቃረብ ነው የተያዘው።  

  አዲሱን “የአምስት ዓመት እቅድ” ለማስተዋወቅ የተለቀቀ ዘፈን! ግጥሙ እንዲህ ይላል፡
                 “If you want to know what China’s gonna do
                  Best pay attention to the shi san wu.”
            በግርድፉ አንተርጉመው ቻይና የምትሰራውን ልወቅ ካሉ የልማቱን እቅድ ልብ ይበሉ
   የቻይና መንግስት፣ አዲስ ዘፈን የለቀቀው ቢጨንቀው ይሆናል። ካለፉት ሦስት ዓመታት ወዲህ፣ የአገሪቱ ኢኮኖሚ፣ እንደ ወትሮው አይደለም። ከ“ሁለት አሃዝ” እድገት ጋር እየተራራቀ ነው። በየዓመቱ ከ10% በላይ የኢኮኖሚ እድገት፣ ከእንግዲህ በቻይና እንደማይደገም፣ የአገሪቱ መንግስት ቁርጡን አውቆ ተናግሯል። በ7% ግን ያድጋል ተብሏል። ይህም ቀላል አይደለም።
ደግሞም፣ ለሰላሳ ዓመታት፣ አስደናቂ እድገት ስትገሰግስ የቆየች አገር ናት። ድንቅ ነው። 10 ሚሊዮን ሰዎች በረሃብ የሞቱባትና በከባድ ድህነት የምትሰቃ አገርኮ እንደነበረች። የያኔው የ‘ሶሻሊዝም’ አባዜ፣ በርካታ አገራትን፣ ቻይናንም ጨምሮ ለባሰ ድህነትና ረሃብ ዳርጓል።
አሃ፣ ሰው፣ በራሱ ጥረት፣ ህይወቱን እንዳያሻሽል የሚከለክል ሶሻሊስት ፓርቲ በገነነበት አገር፤... ሃብት ንብረት ማፍራት “ከሁሉም የከፋ ቁጥር 1 የወንጀል ተግባር ነው” ብሎ የሚያውጅ ሶሻሊስት መንግስት በነገሰበት አገር፣ እንዴት ከድህነት መውጣት ይቻላል? ቻይናም፣ ከዚሁ ታሪክ ቀማሽ ናት።
በ1967 ዓ.ም በኢትዮጵያ የሶሻሊዝም አብዮት ሲታወጅና ንብረት ሲወረስ፤ ቻይና የሶሻሊዝምን መዘዝ ማለትም ድህነትንና ረሃብን እየተጎነጨች ነበረች። የአንድ ቻይናዊ አማካይ የአመት ገቢ፣ 200 ዶላር አይደርስም ነበር (ያው፣ ከኢትዮጵያና ከብዙዎቹ ድሃ የአፍሪካ አገራት የማይሻል)።
ደግነቱ፣ ብዙም ሳይቆይ ነው፣ አንዳንድ የአገሪቱ ባለስልጣናት የባነኑት። “ስራና ኑሮ - በማህበር ብቻ” ብሎ የግል ንብረት እየወረሰ አገርን ማተራመስ እንደማያዋጣ ሲያዩ፣ በዚያው የውድቀት ጎዳና ከመቀጠል ይልቅ፣ ቀስ በቀስ የግል ስራንና የግል ቢዝነስን ለመፍቀድ ለመፍቀድ ወሰኑ። “ሃብታም መሆን፣ ጀግንነት (ቅዱስ) ነው” የሚል መፈክር በየአደባባዩ ወደመዘርጋት ተሸጋገሩ (To be rich is glorious)።
ይህችኑን ‘ሚጢጢ የካፒታሊዝም ቡቃያ’ ትንሽ ትንሽ እያስፋፉ፣ በዚያችው መጠንም እየተሻሻሉ፣ ተዓምረኛውን የእድገት ግስጋሴ ‘ሀ’ ብለው ጀመሩት። ይሄውና ዛሬ፣ የአንድ ቻይናዊ አማካይ የአመት ገቢ፣ ከ7ሺ ዶላር በላይ ሆኗል።
አዎ፤ የተወሰነ ያህል የነፃ ገበያ አሰራርን በማስፋፋት፣ የተወሰነ ያህል አድገዋል። ከዚህ በላይ ለማደግ፣ የነፃ ገበያ አሰራርን ይበልጥ ማስፋፋት እንደሚያስፈልግም አልጠፋቸውም። ግን፣ በፍጥነት ለመራመድ የቻሉ አይመስሉም። የአገሪቱ የኢኮኖሚ እድገት ቀስ በቀስ እየወረደ ነው።
ታዲያ፣ ጉዳቱ፣ ለቻይናዊያን ብቻ አይደለም። የአሜሪካና የአውሮፓ ኢኮኖሚ ሲዳከም፣ አብዛኞቹ አገራት ጉዳት ይደርስባቸው የለ? ምርቶቻቸውን፣ በብዛትና በጥሩ ዋጋ ወደ አሜሪካና ወደ አውሮፓ በመሸጥ፣ የሚያገኙት ገቢ ይቀንስባቸዋል። ልክ እንደዚያው፣ የቻይና ኢኮኖሚ ከተዳከመም፣ እንደወትሮው በፍጥነት ማደግ ካቃተው፣ ጉዳቱ ለሌሎች አገራትም ጭምር ነው።
ምናልባት፣ እንደ በጎ ነገር ሊጠቀስ የሚችለው፤ የቻይና የነዳጅ ፍጆታ ከኢኮኖሚዋ ጋር አብሮ ሲረግብ፣ የአለም የነዳጅ ዋጋ ይቀንሳል። ብዙዎቹ አገራት፣ በዚህ ይፅናኑ ይሆናል። ቻይናዊያንስ? መንግስት በለቀቀው ነጠላ ዜማ።      

               ታላቁ እጣ ሐሙስ ማታ ወጥቷል።
                ከ33 ቢሊዮን ብር በላይ መሆኑ ነው።
                ግማሹን መንግስት በታክስ ቆርጦ ይወስዳል።
                በሎተሪው የማሸነፍ እድል በጣም ትንሽ ነው።
                    300 ጊዜ በመብረቅ የመመታት አደጋ ይበልጣል።
    ከሳምንት ሳምንት የሽልማቱ መጠን እየጨመረ፣ ብዙ ሲወራለት የሰነበተው ታላቁ የአሜሪካ ሎተሪ፣ የ1.6 ቢሊዮን እጣ በማውጣት ሐሙስ ማታ እልባት አግኝቷል።
የሎተሪው ሽልማት ከሦስት ሳምንት በፊት ከ$250 ሚሊዮን በታች ነበር። እጣው ወጣ። ያሸነፈ ሰው አልነበረም። የእጣው ቁጥር ሲታይ፣ ያልተሸጠ ቲኬት ነው። ግን፣ በዚያው ጭጭ ብሎ አይቀርም። በጥቂት ቀናት ውስጥ፣ እጣው እንደገና እንዲወጣ ይደረጋል። እስከዚያው፣ የትኬት ሽያጩ ይቀጥላል - የእጣ ማውጫ ቀን (ሐሙስና ቅዳሜ) ድረስ።
ቀኑ ደርሶ፣ የሎተሪው አንደኛ እጣ ወጣ። ሽልማቱ ወደ 300 ሚሊዮን አድጓል።  ማን አሸንፎ ይሆን? እንደገና አሸናፊ የለም ተባለ። እንዲህ፣ ከሐሙስ ወደ ቅዳሜ፣ ከዚያም ወደ ሃሙስ እየተሸጋገረ፣ የትኬት ሽያጩ እየተስፋፋ፣ ሽልማቱም እያደገ ቀጠለ። ወደ 350 ሚሊዮን ዶላር፣ ወደ 450 ሚሊዮን ዶላር... ብዙም ሳይቆይ ግማሽ ቢሊዮን ደረሰ። ከዚያማ፣ ሳምንት ባልሞላ ጊዜ ውስጥ ነው፤ ከቢሊዮን ዶላር በላይ ለመሄድ የደረሰው - ባለፈው ቅዳሜ።
ትኬት የቆረጡ በሚሊዮን የሚቆጠሩ ሰዎች፣ በጉጉት ቢጠብቁም። በቅዳሜውም እጣ፣ አሸናፊ አልነበረም። ያው፣ ሐሙስን መጠበቅ ነው። ሳይሸጡ የቀሩ ትኬቶች፣ እንደ ጉድ ሲቸበቸቡ... ትናንት በእጣ ማውጫው እለት፣ ሽልማቱ 1.5 ቢሊዮን ዶላር ደረሰ። እጣው ሲወጣም፣ አሸናፊው ቁጥር ታወቀ።

ሎተሪ ማሸነፍና በመብረቅ መመታት
ቲኬት የገዛ ሰው፣ የአንደኛ እጣ አሸናፊ የመሆን እድሉ ምን ያህል ነው? እጅግ በጣም ቅንጣት እድል እንደሆነ ለማሳየት፣ በታላቁ ሎተሪ አሸናፊ የመሆን አጋጣሚን፣ በመብረቅ ከመመታት አጋጣሚ ጋር አነፃፅሮታል - ኤንቢሲ።
እጣው በየእለቱ ቢወጣ እንኳ፣... እርስዎም ሳያዛንፉ በየእለቱ ትኬት ቢገዙ እንኳ፣... በ800ሺ ዓመታት ውስጥ፣ አንዴ ብቻ አሸናፊ ይሆናሉ። በእነዚሁ አመታት ውስጥ ግን፣ 300 ጊዜ በመብረቅ የመመታት አደጋ ይደርስብዎታል።
ሽልማቱም ተቀናሽና ተቆራጭ ይበዛበታል
የ1.5 ቢሊዮን ዶላሩ እጣ ቢያሸንፉ፣ ገንዘቡ ሙሉ ለሙሉ ወደ ባንክ ሂሳብዎ ይተላለፋል ማለት አይደለም።
አንደኛ ነገር፤ ሽልማቱን የሚወስዱት፣ ደረጃ በደረጃ በሰላሳ ዓመታት ነው (በአማካይ፣ በየአመቱ 50 ሚሊዮን ዶላር)።
“ትዕግስት የለኝም፤ አንዴ ሽልማቴን አፈፍ አድርጌ ልውሰድ” የሚሉ ከሆነም ይችላሉ። ነገር ግን፤ 900 ሚሊዮን ዶላር ገደማ ነው የሚደርስዎት።
በእርግጥ፣ ከዚሁም ውስጥ መንግስት የተለያዩ አይነቶ ታክሶችን ይቆርጣል። ቢያንስ ቢያንስ 400 ሚሊዮን ዶላር ያህል ይወስዳል።
ቢሆንም፣ 500 ሚሊዮን ያህሉ የእርስዎ ይሆናል። ‘ኢንቨስት’ ቢያደርጉትና ቢሰሩበት... ይህም ባይሆን፣ እንዲሁ ‘ያለ ሃሳብ’፣ ባንክ ቢያስቀምጡት እንኳ፣ በየአመቱ፣ 20 ሚሊዮን ዶላር ወለድ ያስገኛል። ‘መታደል ነው!’ ያሰኛል።
ግን፣ በርካታ የሎተሪ ባለእድለኞች፣ ያን ያህል ‘እድለኞች’ አይደሉም ይላል ትናንት የወጣው የዩኤስ ቱዴ ዘገባ። አንዳንዶቹ፣ ድንገት እጃቸው የገባው ገንዘብ፣ መጥፊያቸው ይሆናል። እንደ ዘበት የተገኘን ገንዘብ፣ እንደ ዘበት እየበተኑ፣ በአጭር ጊዜ ውስጥ ባዶ እጃቸውን ይቀራሉ። በሶስት ሺ የሎተሪ እድለኞች ላይ የተደረገው ጥናትም፣ የሎተሪ ገንዘብ በሰዎች ኑሮ ላይ ብዙም ለውጥ እንደማያመጣ ያረጋግጣል ብሏል ዩኤስቱዴ። አስር የሎተሪ እድለኞችና ሌሎች አስር ሰዎች... ከጥቂት ዓመታት በኋላ የሚኖራቸውን ኑሮ ብታነፃፅሩ፤ ከሁለቱም ወገን፣ ስኬታማ የሚሆኑ ይኖራሉ፤ ከሁለቱም ወገን ችግረኛ የሚሆኑ ይኖራሉ።    

Saturday, 16 January 2016 10:09

የዘላለም ጥግ

(ስለ ደስታ)

- ደስታን በራስ ውስጥ ማግኘት ቀላል
አይደለም፤ ሌላ ቦታ ማግኘት ደግሞ
አይቻልም፡፡
አግኔስ ሪፕልየር
- ደስታ ልክ እንደ ደመና ነው፤ ለረዥም ሰዓት
ትክ ብለህ ካየኸው ይተናል፡፡
ሳራ ማክላችላን
- ደስታ የሚገኘው በመስጠትና ሌሎችን
በማገልገል ነው፡፡
ሔነሪ ድራሞንድ
- ደስታ በአካል አለመታመም ወይም በአዕምሮ
አለመረበሽ ነው፡፡
ቶማስ ጄፈርሰን
- የተካፈሉት ደስታ ይጨምራል፡፡
ጆስያህ ጊልበርት ሆላንድ
- ራስን መርሳት ደስተኛ መሆን ነው፡፡
ሮበርት ሉዊስ ስቲቨንሰን
- ደስታን መግዛት ነፍስን መሸጥ ነው፡፡
ዳግላስ ሆርቶን
- ፈገግታ አፍንጫህ ስር የምታገኘው ደስታ
ነው፡፡
ቶም ዊልሰን
- ነፃነት ደስታ ነው፡፡
ሱዛን ቢ.አንቶኒ
- ደስተኛ ለመሆን የሚያስፈልግህ ጥሩ
ጠብመንጃ፣ ጥሩ ፈረስና ጥሩ ሚስት ብቻ
ናቸው፡፡
ዳንኤል ቡኔ
- ደስታ ለሰውነት ጠቃሚ ነው፤ የአዕምሮን
ኃይል የሚያጐለብተው ግን ሀዘን ነው፡፡
ማርሴል ፕሮስት
- የደስታ ሁሉ መሰረቱ ጤና ነው፡፡
ሌይግ ሃንት
- በመከራ ወቅት የደስታ ጊዜን ከማስታወስ
በላይ ከፍተኛ ሃዘን የለም፡፡
ዳንቴ አሊግሂሪ