Administrator

Administrator

 ለቤጂንግ 44 አትሌቶች ያሉበት የኢትዮጵያ ጊዜያዊ ቡድን ታውቋል
                               
           9ኛው የዓለም ታዳጊዎች አትሌቲክስ ሻምፒዮና በኮሎምቢያዋ ከተማ ካሊ ባለፈው ሐሙስ ሲጀመር ኢትዮጵያ የመጀመርያ የወርቅ ሜዳልያዋን በ3ሺ ሜትር በማስመዝገብ ጥሩ አጀማመር አሳይታለች። የወርቅ ሜዳልያውን ያገኘችው አትሌት ሹሩ ቡሎ ስትሆን በ3ሺ ሜትር ሴቶች ያሸነፈችው የሻምፒዮናውን ፈጣን ሰዓት በ9 ደቂቃዎች  ከ01.12 ሰከንዶች አስመዝግባ ነው፡፡ በሻምፒዮናው ኢትዮጵያ 10 ሴትና 10 ወንዶች ባካተተ ቡድኗ የምትሳተፍ  ሲሆን ሻምፒዮናው ነገ ሲጠናቀቅ ቢያንስ  9 ሜዳልያዎች ሶስት ወርቅ፤ 3 የብርና 3 የነሐስ እንደምትሰበስብ ግምት አለ፡፡ በዓለም የታዳጊዎች የአትሌቲክስ ሻምፒዮና ላይ ኢትዮጵያን በሁለቱም ፆታዎች የወከሉት 20 አትሌቶች አሰላ ላይ ለሶስተኛ ጊዜ በተደረገው የታዳጊዎች አትሌቲክስ ሻምፒዮና በመሳተፍ ከፍተኛ ውጤት ያስመዘገቡ መሆናቸውን ያስታወቀው ፌደሬሽኑ የወደፊት የአገሪቱን ኮከብ አትሌቶች ለማግኘት ዓለም አቀፍ ውድድሩ ወሳኝ እንደሆነ አምኖበታል። በዓለም አቀፉ የአትሌቲክስ ፌደሬሽኖች ማህበር የሚዘጋጀው የዓለም ታዳጊዎች አትሌቲክስ ሻምፒዮናው በየሁለት ዓመቱ ሲካሄድ በ16 እና 17 ዓመት የእድሜ ክልል የሚገኙ አትሌቶች በሁለቱም ፆታዎች በ40 የውድድር መደቦች ይሳተፉበታል።  ከ800 እስከ ሁለት ሺህ ሜትር  የሩጫና እርምጃ  ውድድሮች የሻምፒዮናው አካል ናቸው፡፡ ከ2 ዓመታት በፊት በዩክሬኗ ከተማ ዶኔትስክ ላይ ተደርጎ በነበረው 8ኛው የዓለም ታዳጊዎች አትሌቲክስ ሻምፒዮና ላይ የኢትዮጵያ ቡድን  ሶስት የወርቅ፣ ሶስት የብር እና ሁለት የነሐስ ሜዳሊያ በመሰብሰብ ከዓለም ሶስተኛ ከአፍሪካ ደግሞ ሁለተኛ ደረጃ ይዞ ማጠናቀቁ ይታወሳል፡፡
በተያያዘ ከወር በኋላ በቻይናዋ ከተማ ቤጂንግ ለሚደረገው 15ኛው የዓለም አትሌቲክስ ሻምፒዮና ኢትዮጵያን ለሚወክለው ቡድን የተመለመሉ አትሌቶች  ጊዜያዊ ስም ዝርዝርን የኢትዮጵያ አትሌቲክስ ፌዴሬሽን ኮሙኒኬሽን ክፍል አስታወቀ።  በነሐሴ ወር አጋማሽ  በሚካሄደው የዓለም አትሌቲክስ ሻምፒዮናው ላይ ኢትዮጵያ በ800 እና 1500 ሜትር መካከለኛ ርቀት፤ በ3ሺ ሜትር መሰናክል፤ በረጅም ርቀት 5ሺ እና 10ሺ ሜትር እንዲሁም በማራቶን ውድድሮች በምትሳተፍበት ቡድን 44 አትሌቶች በጊዜያዊ ስም ዝርዝሩ ገብተዋል፡፡
የኢትዮጵያ አትሌቲክስ ፌዴሬሽን ኮሙኒኬሽን ክፍል ሐምሌ 9/2007 ዓ. ም. ይፋ ያደረገው የዓለም አትሌቲክስ ሻምፒዮና የኢትዮጵያ ቡድን ጊዜያዊ ቡድን የአትሌቶች  ስም ዝርዝር ከዚህ በታች የቀረበው ነው፡፡
በ800 ሜትር በወንዶች መሃመድ አማንና ጀና ኡመር እንዲሁም በሴቶች ሃብታም አለሙ፣ ባይህ ጫልቱ ሹሜ ረጋሳና ኮሬ ቶላ ነገሆ
በ1500  ሜትር በሴቶች ዳዊት ስዩም ፣ ሰንበሬ ተፈሪ ፣አክሱማዊት እምባዬና ጉዳፍ ፀጋዬ እንዲሁም በወንዶች ሱር አማን ወጤ እና መኮንን ገ/መድህን
በ5 ሺ ሜትር ዘጠኝ እንዲሁም በ10ሺ ሜትር ስምንት አትሌቶች በሁለቱም ፆታዎች በጊዜያዊ ዝርዝሩ ተካትተዋል፡፡ በ5ሺ ሜትር ወንዶች ዮሚፍ ቀጀልቻ፣ ሐጐስ ገ/ህይወት ደጀን ገ/መስቀልና የኔው አላምረው ሲሆኑ በሴቶች ደግሞ  አልማዝ አያና፣ ገንዘቤ ዲባባ፣ ሰንበሬ ተፈሪ፣ አለሚቱ ሃዊ  አዝመራ ገብሩ
በ10 ሺ ሜትር ወንዶች ሙክታር አድሪስ፣ ኢማነ መርጊያ፣ ሞስነት ገረመውና  አዱኛ ታከለ፤ በሴቶች ደግሞ ገለቴ ቡርቃ፣ አለሚቱ ሃሮዬ ፣በላይነሽ ኦልጅራ እና  ማሚቱ ዳስካ
በ3000 ሜትር መሠናክል በሁለቱም ፆታዎች ስምንት አትሌቶች ሲያዙ በሴቶች ሕይወት አያሌው፣ ሶፊያ አሰፋ፣ ብርቱካን ፋንቴና ትዕግስት ጌትነት  እንዲሁም በወንዶች ጂክሳ ቶሎሳ፣ ኃ/ማርያም አማረ፣   ታፈሰ ሰቦቃና  ጫላ በዩ
በማራቶን በሴቶች   ትርፌ ፀጋዬ፣ ማሬ ዲባባ፣ ትዕግስት ቱፋ፣ ብርሃኔ ዲባባ  ተይዘው፤ በወንዶች ደግሞ ሌሊሳ ዲሳሳ ፣ የማነ ፀጋዬ፣ ለሚ ብርሃኑ እና እንደሻዉ ካሳ

   በአብያታና ሻላ ሃይቆች በሚገኙት ፓርኮች እና ተራራማ ስፍራዎች የሚካሄደው የኢትዮትሬል የተራራ ላይ ሩጫ ውድድር እድገት በማሳየት ከወር በኋላ እንደሚካሄድ ታወቀ፡፡ ለሯጮች፤ ለተራራ ወጪዎች እና ተጓዦች እንዲሁም ሙሉ ቤተሰብ  አሳታፊ ለሆኑት የኢትዮትሬል  ውድድሮች የዓለም አቀፍ ተሳታፊዎች ጉጉት አስደናቂ ሆኗል፡፡  ዘንድሮ ለሁለተኛ ጊዜ በሚካሄደው  የኢትዮ ትሬል የተራራ ላይ ሩጫ በሶስት ርቀቶች በ42፤ በ21 እና 12 ኪሎሜትሮች ተካፋፍሎ እንደሚካሄድ አዘጋጆቹ ለስፖርት አአድማስ በላኩት መግለጫ አመልክተዋል፡፡ የተራራ ላይ ሩጫው በኢትዮጵያ የስፖርት ቱሪዝምን ለማስፋፋት እና ጤናማ አኗኗርን ለማበረታታት የሚዘጋጅ ነው፡፡ ዘንድሮ በዓለም አቀፉ የትራያል ሩጫ ማህበር አባልነት የተመዘገበው ኢትዮትሬል ከዓለም 50 መሰል ሩጫዎች አንዱ ሆኖም ተጠቅሷል፡፡ ባለፈው ዓመት ውድድሩ ሲካሄድ ከአገር ውስጥ እና ከባህርማዶ እስከ 300 ተሳታፊ ስፖርተኞች እና 2000 ተመልካቾች የነበሩት ሲሆን ዘንድሮ የተሳታፊዎቹን ቁጥር ወደ 800 እንደሚያሳድግና ታዳሚዎቹም ከ3ሺ በላይ እንደሚሆኑ ተጠብቋል፡፡

Saturday, 18 July 2015 11:33

ፀጉርዎ እየሳሳ ነው….?

   የፀጉር መሳሳት የበሽታ ምልክት ሊሆን ይችላል፡፡ የታይፎይድ እጢና የስኳር በሽታዎች የፀጉር መሳሳትን የሚያስከትሉ በሽታዎች ናቸው፡፡ ችግሩ ከመባባሱና አስከፊ ሁኔታ ላይ ከመድረስዎ በፊት ሃኪምዎን ያማክሩ፡፡
አመጋገብዎን ያስተካክሉ፡፡ የተስተካከለ አመጋገብ ጤናዎንና አካልዎን ብቻ ሳይሆን በፀጉርዎ ላይም የራሱን አሉታዊና አዎንታዊ ተፅዕኖዎች ማሳረፍ ይችላል፡፡ ስለዚህም ስለሚመገቡት ምግብ ምንነትና ጠቀሜታ አብዝተው ይጨነቁ፡፡
አዕምሮዎንም ሆነ ሰውነትዎን ያሳርፉ፡፡ ድካምና እረፍት ማጣት የፀጉር መመለጥን (መሳሳትን) ከሚያስከትሉ ምክንያቶች ዋንኞቹ ናቸው። ህይወትዎ ምንም ያህል በውጥረት የተሞላ እንኳን ቢሆን ለራስዎ ጊዜና እረፍት መስጠት ይኖርብዎታል፡፡  እንደ ዮጋና ሜዲቴሽን፣ ያሉ ነገሮች ጭንቀትና ውጥረትን ለማስወገድ እጅጉን ይረዳሉ፡፡ ለፀጉርዎ የሚጠቀሟቸውን ሻምፖና ኮንድሽነሮች እንዲሁም የሚቀቧቸውን ቀለማት ምንነትና አጠቃቀም በደንብ ይረዱ፡፡ በአግባቡ ያልተረዷቸውን ምርቶች ከመጠቀም ይቆጠቡ፡፡
በሻምፖ፣ በኮንድሽነሮችና በፀጉር ማቅለሚያዎች ውስጥ ያሉት ኬሚካሎች የፀጉር መሳሳትና መመለጥን ከሚያፋጥኑ ነገሮች መካከል በግንባር ቀደምትነት ይጠቀሳሉ። ከእነዚህ ይልቅ ተፈጥሮአዊ ይዘታቸውን ያልለቀቁ ንጥረነገሮችን አዘውትረው ይጠቀሙ።

  ወቅቱ ክረምት ነው፡፡ ልጆች የዓመቱ ትምህርታቸውን አጠናቀው እረፍት የሚያደርጉበት ጊዜ፡፡  በዚህ የክረምት ወቅት ልጆች እንደየአካባቢያቸው፣ እንደየቤታቸውና እንደየልማዳቸው የእረፍቱን ጊዜ የሚያሳልፉባቸው መዝናኛዎች አሏቸው፡፡
በአሁኑ ጊዜ እንደ አዲስ አበባ ባሉ ከተሞች በስፋት እየተለመዱ ከመጡ የልጆች መዝናኛዎች መካከል ፊልሞች፣ ጌሞችና ፕሌይ ስቴሽኖች ይጠቀሳሉ፡፡
በተለይ የተለያዩ ጌሞችን ከኢንተርኔት በቀጥታ በመውሰድ ልጆች በስልኮች፣ በላፕቶፖችና በቲቪ ስክሪኖች ጭምር እንዲጫወቱበት ማድረግ እየተለመደ መጥቷል፡፡
ይሁን እንጂ እነዚህ ጌሞች ከመዝናኛነት ባለፈ ልጆችም ትምህርት የሚያገኙባቸው እንዲሆኑ ማድረግ ያስፈልጋል፡፡ ለልጆችዎ የሚመርጧቸው ጌሞች ቀለል ባለ መልኩ ህፃናት እየተዝናኑ እንዲማሩባቸው ሆነው የተዘጋጁ ሊሆኑ ይገባል። ለህፃናት በሚመች መልኩ የተሰሩና ህጸናትን እያዝናኑ ለመማር ያስችላሉ የሚባሉ ጌሞችን ከያዙ ድረ-ገፆች መካከል ጥቂቶቹን እነሆ፡-
Learning games for kids
በዚህ ዌብሳይት ላይ ያሉት ጌሞች በተለያዩ ዝርዝር ጉዳዮች የተከፋፈሉ ናቸው
Educational songs and videos
የህፃናት መዝሙሮችንና ሳይንስና ምርምር ነክ የሆኑ ነገሮችን ቀለል ባለ ሁኔታ የሚያስረዱና ዝግ ባለ እንቅስቃሴ የተዘጋጁ ቪዲዮዎች የሚገኙበት ክፍል ነው፡፡    
Health games
ልጆች ስለ አለርጂክ፣ ስለ ጥርስ ጤና አጠባበቅ፣ ስለ ጤናማ ሰውነት አቋም እንዲያውቁ የሚያግዙ መረጃዎችን በአዝናኝ መንገድ ያቀርባል፡፡  
Maths games
ልጆች በጨዋታ መልክ ስለ ሂሳብ ጠቃሚ ዕውቀቶችን የሚገበዩበትና የሂሳብ ችሎታቸውን የሚያሻሽሉበት ጌሞችን የያዘ ክፍል ነው፡፡
Geography games
ልጆች የተለያዩ የዓለም ክፍሎችን እንዲያውቁ የሚረዱ ጌሞች የተካተቱበት ነው፡፡
Science games
በእንስሳት፣ በተፈጥሮና፣ በህዋ ላይ ባሉ ሳይንሳዊ እውነታዎች ላይ ተመስርተው የተሰሩና ለልጆች መሠረታዊ ዕውቀትን የሚያስጨብጡ ጌሞች ያሉበት ነው፡፡
Keyboarding games
ልጆች በኮምፒዩተር የመፃፍ ችሎታቸውን እንዲሁም የቋንቋ ዕውቀታቸውን ለማዳበር የሚያስችላቸውና ጥሩ ክህሎትን የሚጨብጡበት ጌሞች የሚገኙበት ክፍል ነው፡፡
Miscellaneous games  
እኒህ ልጆችን እያዝናኑ የሚያስተምሩ ልዩ ልዩ ጨዋታዎችን ያካተቱ ጌሞች ናቸው፡፡
Pre-school games  
በአፀደ ህፃናት ደረጃ ላይ ያሉ ህፃናትን እያዝናኑ የሚያስተምሩ ጌሞች ይገኙባቸዋል፡፡
ወላጆች፡- ልጆቻችሁ አልባሌ ፊልሞችን እያዩ ጊዜያቸውን ከሚያጠፉ እንዲህ ዓይነት ጌሞችን በመጫን፣ የእረፍት ጊዜያቸውን የትምህርትና የመዝናናት ብታደርጉላቸው አይሻልም?! 

      በእስልምና ውስጥ በከፍተኛ ድምቀት የሚከበሩ ሁለት ኢዶች (በአሎች) አሉ፡፡ የመጀመሪያው የረመዳን ፆምን ማብቃት የሚያበስረው ኢድ - አልፈጥር ሲሆን፣ ሁለተኛው ደሞ ከሁለት ወራት በኋላ የሐጂ ስነ - ስርዓትን ተከትሎ የሚመጣው ኢድ - አልአድሓ (የእርድ በዓል ነው፡፡ ረመዳን ተጠናቆ የምናከብረው በዓል ኢድ አልፈጥር) ስለሆነ እኔም የማወራችሁ ስለዚሁ ክብረበዓል አጠቃላይ ገፅታ ነው፡፡
ረመዳን፤ ሙስሊም ምእመናን ራሳቸውን የሚያንፁበት፣ ወደ አምላክ የሚቀርቡበት የኢማን እውቀታቸውን የሚያሳድጉበት ልዩ የፆም ወር ነው። የረመዳን ወር ከሌሎቹ ወራቶች የተለየና  ትልቅ የሚያደርገው፣ ምእመናን ፀሐይ ከመውጣቷ በፊት አንስቶ እስከ ጠለቀችበት  ድረስ ከምግብ፣ ከውሐ፣ ከወሲብ ግንኙነት (ህጋዊ ትዳርን ጨምሮ)፣ ከመጥፎ ንግግር እና ባህሪ የተቆጠቡ መሆን ስላለባቸው ነው፡፡ በእርግጥ ህጋዊ ያልሆነ ወሲብን ጨምሮ ሌሎቹ መጥፎ ባህሪያት በሌላው ወር ይፈቀዳል ማለት አይደለም፡፡ ነገር ግን የወሩን ታላቅነት አፅንኦት ለመስጠት አላህ የደነገጋቸው ህጎቹ ናቸው። በተጨማሪም 30 ጁዝ (ምዕራፍ) የያዘውን ቅዱስ ቁርአንን ምዕመናን በረመዳን አንብበው የሚያጠናቅቁበት ወር ነው፡፡
የረመዳንን ወር ከአንድ አነስተኛ የማሰልጠኛ ተቋም ጋር ማመሳሰል እንችላለን፡፡ በአንድ ማሰልጠኛ ተቋም ውስጥ የሆነ ዘርፍ አጥንተን እውቀትና ስነ - ምግባሮች እንደምንጨብጠው ሁሉ፤ በረመዳን ወቅትም በቁርአን እውቀት አዕምሯችንን አበልፅገን፣ በመንፈሳዊ እሴቶች ተሐድሶ ወስደን የምንወጣበት ወር ነው፡፡ ወይም ደግሞ በአንድ ወታደራዊ ካምፕ ውስጥ ሰልጣኞች አካላቸውን ለማፈርጠም እና የሰውነታቸውን ጥንካሬ ለማረጋገጥ የተለያዩ ስልጠናዎችን እንደሚወስዱት ሁሉ፤ በረመዳንም ምእመናን መንፈሳዊ ጥንካሬን ለማግኘት እምነቱ የሚያዘውን አመጋገብ ዘይቤ ይለውጣሉ፡፡ እንዲሁም በረመዳን ወር ብቻ የሚገኙ ሃይማኖታዊ ስልጠናዎችን ተግብረው ቀሪውን ህይወታቸውን ከፈጣሪ ጋር ለማቀራረብ ይሞክራሉ፡፡ በጎ ስራዎችን ማሳደግ እና የአምልኮ ስርአቶችን በብዙ መፈፀም ሌሎቹ የስልጠና ግብአቶች ናቸው፡፡
ራሳችንን ከምግብና ከውሃ ማቀብ፣ በድህነት ለሚኖሩ ሚስኪኖች እንድናስብ ያደርገናል፡፡ ምግብና ውሃ አጥቶ መኖር ምን እንደሚመስል የምናውቀው በረመዳን ወር ነው፡፡ ምግብና ውሃ ብቻ ሳይሆን ሌሎች የቅንጦት ነገሮችን ማጣት ያለውን ስሜት በረመዳን ወር ፍንትው ብሎ ይታየናል፡፡ ራስን ዝቅ አደርጎ ለፈጣሪ መስገድ ያለውን እርካታ ረመዳን ይነግረናል፡፡ ማፍጠሪያ ሰዓት ደርሶ ከቤተሰብ እና ከወዳጆች ጋር ተሰብስቦ አብሮ መብላት ራሱን የቻለ የማህበራዊ በጎ እሴት ነው፡፡ ከነዚህ ስልጠናዎች በኋላ የሚቀረን ተመርቆ ከስልጠናው መሰናበት ነው፡፡ የረመዳን ምረቃ ደግሞ ኢድ - አልፈጥር ነው። ምእመናን ኢድ - አልፈጥርን በማክበር ከረመዳን ስልጠናዎች ተመርቀው ይወጣሉ፡፡
ኢድ - አልፈጥር ትርጉሙ ራሱ የፆም ማጠናቀቂያ ክብረ - በአል እንደማለት ነው፡፡ በአብዛኛው “የአለም ሀገሮች ውስጥ ለ3 ቀናት በድምቀት ይከበራል፡፡
ኢድ አልፈጥር በብዙ ሀገሮች በተለያዩ መንገዶች ቢከበርም የጋራ የሆነ አንድ ነገርን ይዟል፡፡ ይሄውም በበአሉ ቀን ሁሉም አማኞች በጧት ተነስተው ልዩ የሶላት ስግደት ወደሚደረግበት ቦታ ይተማሉ። በኛ ሀገር ምእመናን በለሊት 11 ሰዓት ተነስተው ወደ ስግደት ከመሄዳቸው  በፊት ተሰብስበው ገንፎ በቅቤ ወይም በተልባ ይበላሉ፡፡ አሁን አሁን ብዙም ባይስተዋልም እንጀራ በፌጦ የመጉረስ ልማድ ነበር። (በሀገራችን ለዘመን መለወጫ መስከረም ላይ እንደሚደረገው አይነት)
የኢድ-አልፈጥር ስግደት የሚደረገው በመስጂድ ውስጥ ወይም ሁሉንም አማኝ ሊያሰባስብ በሚችል አንድ ገላጣ ቦታ ላይ ነው፡፡ የእምነቱ ተከታዮች በቡድን እየሆኑ ተክቢራ በማድረግ (የበአሉ የውዳሴ ዜማዎች) ወደ ስግደቱ ቦታ ይተማሉ፡፡ በሀገራችን ውስጥ ሙስሊሞች ከተለያዩ አቅጣጫዎች በቡድን እየሆኑ፣ ተክቢራ እያደረጉ ወደ ስታዲየም እንደሚሄዱት ማለት ነው፡፡
ከስግደት መልስ ምእመናን የበአል ድግስ አድርገው ከቤተሰብ፣ ከዘመድ - አዝማድ እንዲሁም ከጐረቤት ጋር በአሉን በደስታ ያሳልፋሉ፡፡ ቤተ ዘመዶችን እየዞሩ መጠየቅና እንኳን አደረሳችሁ ማለት የኢድ አልፈጥር ልዩ ባህሪው ነው፡፡ የምግቡ አይነት እንደየባህሉ ከሀገር ሐገር ቢለያይም፣ ልዩ ምግቦችን ማዘጋጀት ግን የማይቀር ጉዳይ ነው። በተለይ ህፃናቶች በኢድ አልፈጥር ጊዜ በአዲስ ልብሶች አጊጠው በዘመድ አዝማድ ቤቶች እየዞሩ “የሚናኢድ” በማለት ሳንቲሞችን ይቀበላሉ፡፡ ይህ በአል በህፃናቶች ዘንድ ልዩ በመሆኑ ከቤተሰብና ከዘመድ አዝማድ የሚሰበሰቡት ሳንቲሞች በጣም ብዙ ናቸው፡፡
አንድ ሙስሊም በረመዳን ማፍጠሪያ ወቅት ምጽዋት ያልሰጠ ከሆነ የኢድ አልፈጥርን በአል ተጠቅሞ ለሚስኪኖች ዞካ መስጠት አለበት፡፡ የምግብ አልያም የገንዘብ ስጦታ ሊሆን ይችላል፡፡ ብዙ ሙስሊሞች የበአል ድግስ አድርገው ደሐዎችን ያበላሉ፡፡ አንዳንዶች ደግሞ የታረዙትን ያለብሳሉ፡፡ ምንም ይሁን ነገር ግን በኢድ አልፈጥር በአል ወቅት ለድሐዎች የምጽዋት እጆችን መዘርጋት ሐይማኖቱ የሚመክረው በጐ ተግባር ነው፡፡ መልካም የኢድ አልፈጥር በአል ለመላው የእስልምና ተከታዮች በሙሉ እንዲሆን እየተመኘሁ እሰናበታለሁ፡፡  

Saturday, 18 July 2015 11:23

የፀሐፍት ጥግ

(ስለ ንባብ)
- ግሩም መፅሐፍ መጨረሻ የለውም፡፡
አር.ዲ. ከሚንግ
- ባህልን ለማጥፋት መፃህፍትን ማቃጠል
አያስፈልግም፡፡ ሰዎች ማንበብ እንዲያቆሙ ብቻ
ማድረግ በቂ ነው፡፡
ሬይ ብራድበሪ
- መፅሃፍ በእጅህ የምትይዘው ህልም ነው፡፡
ኔይል ጌይማን
- ሁሉም ሰው የሚያነባቸውን መፃህፍት ብቻ
የምታነብ ከሆነ፣ ሁሉም ሰው ከሚያስበው
ውጭ አታስብም፡፡
ሃሩኪ ሙራካሚ
- ራስህ የማታነበውን መፅሃፍ ለልጅ አለመስጠትን
መመሪያህ አድርገው፡፡
ጆርጅ በርናርድ ሾው
- በመፃህፍት ካልተከበብኩ በቀር እንቅልፍ
መተኛት አልችልም፡፡
ጆርጅ ሉዊስ ቦርጅስ
- መፅሃፍ ምናብን የሚያቀጣጥል መሳሪያ ነው፡፡
አላን ቤኔት
- የሰው ማንነት በሚያነባቸው መፃህፍት
ይታወቃል፡፡
ራልፍ ዋልዶ ኤመርሰን
- መፅሃፍ ስታነቡ ፈፅሞ ብቻችሁን አይደላችሁም።
ሱሳን ዊግስ
- ጥቂት ገንዘብ ሳገኝ መፃህፍት እገዛበታለሁ፡፡
ከዚያ ከተረፈኝ ምግብና አልባሳት እሸምታለሁ፡፡
ኢራስመስ
- እንደ መፅሃፍ ያለ ታማኝ ጓደኛ የለም፡፡
ኧርነስት ሄሚንግዌይ
- የምናነበው ብቻችንን አለመሆናችንን ለማወቅ
ነው፡፡
ሲ.ኤስ.ሌዊስ
- አሮጌውን ኮት ልበስና አዲሱን መፅሃፍ ግዛ፡፡
ኦዩስቲን ፉልፕስ
- ብዙ አንብቦ ትንሽ ከማሰብ፣ ትንሽ አንብቦ ብዙ
ማሰብ ይሻላል፡፡
ዴኒስ ፓርስንስ ቡርኪት
- ህፃናት አንባቢያን የሚሆኑት በወላጆቻቸው
ጭን ላይ ነው፡፡
ኢሚሊ ቡችዋልድ
- ንባብ ዘላቂ ደስታ ያጎናጽፋችኋል፡፡
የአሜሪካ ቀዳሚ እመቤት ላውራ ቡሽ
- ሁሉም አንባቢያን መሪዎች አ ይደሉም፤ ሁ ሉም
መሪዎች ግን አንባቢያን ናቸው፡፡
ሐሪ ኤስ. ትሩማን
- ንባብን ማስተማር ሮኬት ሳይንስ ነው፡፡
ሉዊስ ሞትስ
- የዛሬ አንባቢ፣ የነገ መሪ ነው፡፡
ማርጋሬት ፉለር
- በልጅ ህይወት ውስጥ መፃህፍትን የሚተካ
የለም፡፡
ሜይ ኤለን ቼስ

እንዴት ሰነበታችሁሳ!
ኢድ ሙባረክ!
ሰውየው ጓደኛው ዘንድ ስልክ ደውሎ እንዲህ ይለዋል፡፡ “ምክር ከፈለግህ የጽሁፍ መልእክት ላክልኝ፣ ጓደኛ ከፈለግህ ደውልልኝ፣ እኔን ከፈለግኸኝ ወደ እኔ ና…ገንዘብ ከፈለግህ ግን የደወሉላቸውን ደንበኛ አሁን ማግኘት አይችሉም…” ብሎ ዘጋው፡፡
ስሙኝማ…ጓደኝነት፣ ወዳጅነት ምነዋ እንዲህ ቅጡን አጣ! የምትሰሙት ሁሉ አገር ታምሶ ወዳጅነቶች… ወደ ደመኛ ጠላቶች ስለተለወጡ ‘ቤስት ፍሬንዶች’… ምናምን ሺህ ብር አብሮ አደጉ ስለካደው ምስኪን…ምን አለፋችሁ… “ዓለም የትያትር መድረክ ናት…” የሚለው ላይ…አለ አይደል…ለእኛ አገር “…ያውም የትራጄዲ!” የሚለውን ልትጨምሩ ምንም አይቀራችሁ፡፡
ከምር የሆነ ነገር ነው፡፡ ሰውየው ለሁለት ወር ወርክሾፕ ወደ አንድ አፍሪካ አገር ሄዶላችኋል፡፡ ቤት ውስጥ ከሚስቱ በስተቀር ሌላ ሰው የለም፡፡ እናላችሁ…¸የልብ ጓደኛ ሆዬ የወዳጁ ሚስት ብቻዋን እንዳትሆን በማለት መለስ ቀለስ ሲል ‘አንዱ ነገር ወደ ሌላ እየመራ’ ተቀምጠው የሚያወሩ የነበሩት ጋደም ብለው ‘ወደ መወያየት’ ጀመሩላችሁ፡፡
ሰውየው ተመልሶ ሲመጣ ማን እንደነገረው ሳይታወቅ ጉዱን ይሰማል፡፡ ምንም ሳያቅማማም ፍቺ ጠይቋል አሉ፡፡ የተሻሻለ ዘመን… እንደ በፊቱ ቢሆን ለየጓደኛው እየደወለ… “ስማ አንድ ማካሮቭ ወይም ኮልት ሽጉጥ ምናምን የሚገኝበት ታውቃለህ…” ምናምን ይል ነበር፡፡ እኔ የምለው… እንትናዬዎች ሰይፍ ማማዘዝ ተዉ ማለት ነው!  ቂ…ቂ…ቂ…
ስሙኝማ…በፊት እኮ እንትናዬን ለጓደኛ በአደራ መስጠት ይህን ያህል ስጋት አልነበረውም። እንደውም አንዱ የታማኝ ጓደኛ መገለጫ የዚህን አይነት አደራ መጠበቅ ነው፡፡ የድሮ የልብ ጓደኛ እኮ ጓደኛው ርቆ ሲሄድ እንትናዬውን በአደራ ይጠብቅ ነበር፣ አሁን ግን ጓደኛ በበር ሲወጣ ‘ቤስት ፍሬንድ’ በመስኮት ሳይሆን በዛው በር የሚገባበት ዘመን ነው።
እግረ መንገዴን ይቺን ስሙኝማ፡፡ ሁለቱ ጓደኛሞች ሲጠጡ አምሽተው ዘጠነኛው ደመና ላይ ወጥተዋል፡፡ እናማ… በጨዋታ መሀል ምን ይላል…
“ስማ፣ አንድ የምነግርህ ነገር አለ፡፡ ግን ቅር አይልህም አይደል!”
“ለምንድነው ቅር የሚለኝ! “ስለ ሰው ቀድጄ ልልበሰው…” አይነት ነገር ይናገራል፡፡ ጓደኝየውም…
“ይሄን ስነግርህ አዝናለሁ፡፡ ሚስትህ ግን ለትዳሯ ታማኝ አይደለችም፣” ይላል፡፡ ሰውየው ምን ብሎ ቢመልስ ጥሩ ነው…
“እሷ ሴትዮ በቃ አትሻሻልም! አንተንም ሸወደችህ ማለት ነው?” ብሎት እርፍ፡፡
ቤንጃሚን ፍራንክሊን የሚሉት ሰው… “ሦስት ታማኝ ጓደኞች አሉ፡፡ ያረጀች ሚስት፣ ያረጀ ውሻና፣ በእጅ ያለ ገንዘብ…” ብሏል አሉ ፡፡
ታዲያላችሁ…“የልብ ጓደኛዬ፣ የክፉ ቀኔ…” ምናምን ማለት እያስቸገረ ያለበት ዘመን ነው፡፡
ዘንድሮ ‘ጉድና ጅራት’ ወደኋላ መሆኑ ቀርቶ ፊት ለፊት በሆነበት ዘመን የጥንት የልብ ጓደኛ ማግኘት ደስ ይላል፡፡ ቢያንስ ቢያንስ የሚወራ አይጠፋም። እናላችሁ… እንዲሁ በየኮብልስቶኑ ላይ ዘንበል፣ ዘንበል ስትሉ የጥንት ጓደኛችሁን ታገኛላችሁ፡፡ እናላችሁ ነገርዬው ይሄኔ ነው፡፡
“አንተ! የሚገርም ነው፡፡ አንድ ሀያ ምናምን ዓመት አይሆነንም!” ምናምን እያላችሁ በሰከንድ አሥራ ስምንት ጥይት ትለቃላችሁ፡፡
እሱ ሆዬ… አለ አይደል… መጀመሪያ ትኩር ብሎ ያያችኋል፡፡ ለማስታወስ ግራ የተጋባ ይመስል መልስ ሳይሰጥ ያያችኋል፡፡ እናንተም… “ረሳሁህ እንዳትል…” አይነት ነገር ትሉና “ኮከበ ጽባሀ ሁለተኛ ደረጃ…” ምናምን እያላችሁ መዝገብ መግለጥ ትጀምራላችሁ። አሁንም እንደነገሩ ያያችኋል፡፡ ብዙ ቆይቶ ትዝ ይበለውም፣ አይበለውም…“ኦ!” ይልና ከእጁ ሦስቷን ጣት ያቀረብላችኋል፡፡ እመኑኝ…ይሄ የጥንት ጓደኛችሁ ወይ ገንዘብ አግኝቷል፣ ወይ ወንበር አግኝቷል፡፡ ዘንድሮ ያስቸገሩን ሁለት ነገሮች ቢኖሩ ገንዘብና ወንበር ናቸው፡፡
እናላችሁ… “የጥንት ጓደኛዬ፣ አብረን እኮ ስንትና ስንት አድቬንቸር አሳልፈናል!” አይነት ትዝታ እየጠፋ ነው፡፡
የዘንድሮ ጓደኝነት ደግሞ የሚመሰረተው በአድቬንቸር ምናምን ሳይሆን በገበያው ሁኔታ ነው፡፡ ለጓደኝነት ለመመረጥ ‘በገበያው ላይ’ ያላችሁ ዋጋ መታወቅ አለበት፡፡ እንደ አክስዮን ገበያው ‘ዋጋችሁ’ ዝቅ ሲል “መንገዱን ጨርቅ ያድርግልህ…” ትባላላችሁ፡፡
እናላችሁ…የዘንድሮ ‘ቤስት ፍሬንድነት’ አንጻራዊ ነው፡፡ በቃ ወረቀት ላይ ያልሰፈረ ኮንትራት በሉት፡፡
ሰውየው ምን አለ አሉ መሰላችሁ… “ዕድሜው ከ30 ዓመት በላይ የሆነ ሰውን ምን ያህል ጓደኛ እንዳለው ጠይቀው፡፡ ከአሥር በላይ ብሎ ከመለሰልህ የቆጠረው ጓደኞቹን ሳይሆን የሥራ ባልደረቦቹን ነው፡፡” እንዴት ሸጋ አባባል ነች!
ስሙኝማ…የልብ ጓደኞች የምንባለው እኰ ድሮ የምናወራውና አሁን የምናወራው ተለውጧል፡፡ በፊት እኮ…“ስማ ያቺ የኮተቤዋን፣ ያቺ እንኳን የቀበሌ ድንኳን በሚያክለው ቀሚሷ ስር ሁለት ሱሪ ትለብስ የነበረችው… አይተኸት ታውቃለህ!” ሲባል… “የእኔ ጌታ የሆነ ባለጊዜ ጠብ አድርጋ አሁን በአጠገቧ እንኳን አታልፍም አሉ…” አይነት የጋራ አጀንዳ ነበር።
ደግሞላችሁ… ገርልዬዋን የእንትን ሰፈር ልጆች ለክፈዋት ስለተካሄደው ክትክት…አንድ ትሪ ድንች ለሦስት ተበልቶ ስለማይጠገብበት…“አንድ በራድ” ሲባል የቀዘቀዘ ሻይ ስላቀረበው አስተናጋጅ… አንድ ብር ይዞ ባሻ ወልዴ ችሎት ብቅ ብሎ “ሀምሳ ሳንቲም ጨምር…” ተብሎ ሲሮጥ ስለመጣው ጩኒ… መአት የሚወራ ነገር ነበር፡፡
ዘንድሮ ግን ድሮ ምናምን ቀርቶ ከአሥራ እምስት ዓመት በኋላ ስትገናኙ የመጀመሪያው ዓረፍተ ነገር “አሁን ይቺ አገር ነች!” ምናምን አይነት ብሶት ነው። ምን አለፋችሁ…በቅጡ እንኳን የወዳጅነት ሰላምታ ሳንለዋወጥ… “ስማ በሻይ ጠቅሰን የምንበላው ዳቦ እንኳን እንዲህ ይወደድ!” እንባባላለን፡፡
እግረ መንገዴን የሆነች ያነበብኳት ነገር ትዝ አለችኝማ…
እሱና እሷ ተጋብተው የሠርጉ ስነ ስርአት ካለፈ በኋላ ሚስት አንድ መለስተኛ ሳጥን አልጋዋ አጠገብ ታስቀምጣለች፡፡ ለባሏም በምንም አይነት ሳጥኑን እንዳይከፍት ታስጠነቅቀዋለች፡፡ አርባ ዓመታት አለፉ፡፡ አንድ ቀንም አቶ ባል ነገሩ ይከነክነውና ሚስቱ ሳታውቅ ሳጥኑን ይከፍተዋል፡፡ ውስጡም ሦስት ባዶ የቢራ ጠርሙሶችና አንድ መቶ አርባ ሺህ ዶላር ያገኛል፡፡ ማታም ባል ሚስቱን “የእኔ ውድ አዝናለሁ ግን ሳጥኑን ከፍቼ ነበር፡፡ ሦስቱ ባዶ የቢራ ጠርሙሶች ምንድናቸው?” ይላታል። ሚስትም…
“ከሌላ ወንድ ጋር በተኛሁ ቁጥር አንድ ቢራ እጨልጥና ባዶውን ጠርሙስ ሳጥኑ ውስጥ አስቀምጠዋለሁ፣” ትለዋለች፡፡
ባልየውም ትንሽ ያስብና ‘በአርባ ዓመት ሦስት ጊዜ ብቻ መማገጥ ምንም አይደለም’ ብሎ ራሱን ያሳምናል፡፡ ቀጥሎም…
“እሺ፣ የጠርሙሶቹስ ይሁን፡፡ አንድ መቶ አርባ ሺህ ዶላሩን ምን ስትይ አጠራቀምሽው?” ይላታል፡፡ ሚስት ምን ብትለው ጥሩ ነው…
“ሳጥኑ ሦስት ጠርሙስ ይዞ ተጨማሪ ጠርሙስ አላስገባ ሲለኝ ባዶ ጠርሙሶችን በገንዘብ እየለወጥኩ ያስቀመጥኩት ነው…” ብላው አረፈች፡፡
ሰውየው የተዋሰውን የጓደኛውን መኪና ያጋጫል፡፡ ማታ ቤት ሲገባ ሚስቱ…
“መኪናው መገጨቱን ጓደኛህ ሲያይ ምን አለህ?” ትለዋለች፡፡
“ስድብ ስድቡን ትቼ ሌላውን ብቻ ልንገርሽ?”
“አዎ፣ ስድቡን ተወውና ሌላውን ንገረኝ፡፡”
“እንግዲያው ምንም ነገር አላለም፡፡”
ዘንድሮም ‘ስድብ፣ ስድቡን’ ስናወጣ ባዶ የሚሆኑ ንግግሮች፣ መግለጫዎች፣ ማብራሪያዎች መአት ናቸው፡፡
እናላችሁ… “ጓደኛ አታሳጣኝ…” ማለት ዘንድሮ ነው፡፡
እውነተኛ የልብ ጓደኞችን ያብዛላችሁማ!
ደህና ሰንብቱልኝማ!

ፎከር - 50 ለመጨረሻ ጊዜ የተመረተው ከ20 ዓመት በፊት ነው

   በኢትዮጵያ የሚንቀሳቀሱ የአየር ትራንስፖርት አገልግሎት ሰጪዎች፤ ከ50 ሰው በላይ እንዳያጓጉዙ የተጣለባቸው ገደብ ሊያሰራቸው እንዳልቻለ ጠቁመው ገደቡ እንዲነሳላቸው ጠየቁ፡፡  
የበረራ አገልግሎት ሰጪዎቹ፤ ከዚህ ቀደም የወንበር ገደቡን ጨምሮ የጋራዥ ቦታና ሌሎች በዘርፉ የሚታዩ ችግሮች ለስራቸው መሰናክል እንደሆኑባቸው ሲገልፁ ቆይተዋል፡፡
የናሽናል ኤርዌይስ ባለቤትና ስራ አስኪያጅ ካፒቴን አበራ ለሚ ለአዲስ አድማስ  እንደተናገሩት፤ በአሁኑ ወቅት ከ79 ሰው በታች የሚጭን አውሮፕላን ገበያ ላይ የለም፡፡ በተለምዶ ፎከር - 50 በሚል የሚጠሩትና 50 ሰዎችን የሚጭኑት አውሮፕላኖች ለመጨረሻ ጊዜ የተመረቱት ከ20 ዓመታት በፊት ነው፡፡
“79 ሰው የሚጭነውን አውሮፕላን ገዝቶ 50 ሰው መጫን ኪሳራ ነው” ያሉት ካፒቴኑ፤ የወንበር ገደቡ ሊያሰራን ስላልቻለ ሊነሳ የሚችልበት መንገድ ቢኖር የግል የአቬሽን ዘርፍን ወደ አንድ ደረጃ ያሳድገዋል ብለዋል፡፡
በቅርቡ ኢትዮጵያ የዓለም ምርጥ የቱሪዝም መዳረሻ ተብላ መመረጧን ያስታወሱት ካፒቴን አበራ፤ በወንበር ገደቡ ምክንያት ወደ ሃገሪቱ በብዛት እየጐረፉ ያሉትን ቱሪስቶች ለማስተናገድ እንዳልቻሉ ተናግረዋል፡፡ ገደቡ እንዲነሳ በተደጋጋሚ ጥያቄ ማቅረባቸውን አስታውሰውም፣ ይነሳል እየተባለ ሶስት ዓመታት ያለ ውጤት ማለፉን ገልፀዋል፡፡
ከወንበር ገደቡ በተጨማሪም በቦታ ችግር የተነሳ፣ የሰው ሃይሉ እያለ አውሮፕላን የሚያሰሩት ደቡብ አፍሪካ ድረስ በመሄድ መሆኑን ጠቁመው፤ ይሄም ነዳጅን ጨምሮ ለተለያዩ ወጪዎች እየዳረጋቸው እንደሆነ ካፒቴኑ ገልፀዋል፡፡
በአቬሽን ዘርፍ ለረዥም ዓመታት ያገለገሉት አቶ ስንታየሁ በቀለ በበኩላቸው፤ በአሁኑ ወቅት በየትኛውም አገር የወንበር ገደብ እንደሌለ ገልፀው፣ የገደቡ መነሳት ለአገሪቱ ኢኮኖሚ እድገት ከፍተኛ ሚና እንደሚኖረው ተናግረዋል፡፡
ኢትዮጵያ እያደገች ያለች አገር በመሆኗ የኢኮኖሚ እድገቷን ተከትሎ የቱሪስት ፍሰቱም ስለሚጨምር ቱሪስት የማስተናገድ አቅሟን ልትጨምር እንደሚገባ አቶ ስንታየሁ ያስረዳሉ፡፡ ኢትዮጵያ በአቬሽን ኢንዱስትሪው መልካም ስም ከተቀዳጁ አገራት መካከል አንዷ በመሆኗ በዘርፉ የሚታዩ ችግሮችን ፈትቶ፣ የግሉን ዘርፍ በመደገፍ የአቬሽን ዘርፉን ማሳደግ እንደሚቻል ጠቁመዋል፡፡
የወንበር ገደብ መነሳቱ የተሻሉ አውሮፕላኖችን ለማስገባት እድል ስለሚፈጥር ቱሪስቶች ደረጃውን የጠበቀ አገልግሎት እንዲያገኙ ያስችላቸዋል ያሉት አቶ ስንታየሁ፤ ቱሪስቶቹ በትናንሽ /ቻርተር/  አውሮፕላኖች የሚጠየቁት ከፍተኛ ክፍያም እንደሚቀንስላቸው አብራርተዋል፡፡

• ስጋት ከተጋረጠባቸው 14 ሀገራት ውስጥ ተካታለች
• ሴኔጋል፣ ታንዛኒያ፣ ኡጋንዳ፣ሞዛምቢክ በዕዳ ተዘፍቀዋል

      የውጪ ብድር እዳ ኢኮኖሚያቸውን ሊፈታተን ይችላል የሚል ስጋት ከተጋረጠባቸው 14 የአለም
አገራት ኢትዮጵያ አንዷ መሆኗን ዘ ጋርዲያን የአለም ባንክን ሪፖርት ጠቅሶ ዘግቧል፡፡ በአሁን ወቅት ኢትዮጵያ ከፍተኛ የብድር እዳ እንዳለባት የጠቀሰው ሪፖርቱ፤ ከአጠቃላይ አገራዊ ምርቷ 45 በመቶ የሚሆነው ከብድር የተገኘ ገንዘብ እንደሆነ ጠቁሞ፤ በጥቂት ጊዜያት ውስጥ ይህ አኃዝ ወደ 65 በመቶ ሊያሻቅብ እንደሚችል ጠቁሟል፡፡ ከለጋሽ ተቋማትና ሃገራት የሚገኝ ብድር ለአጠቃላይ አገራዊ ምርት ያለው አስተዋጽኦ ከ30 በመቶ በላይ ከሆነ ሀገራት ወደ ከፍተኛ የእዳ ቀውስ እያመሩ መሆኑን እንደሚያመለክት የጠቆመው ሪፖርቱ፤ ኢትዮጵያም በዚህ የአደጋ ቀጠና በከፍተኛ ደረጃ ከገቡ 14 የአለም  ሀገሮች መካከል ተጠቅሣለች።  ከፍተኛ የውጭ እዳ ውስጥ ተዘፍቀዋል የተባሉት 14 ሀገራት ኢትዮጵያን ጨምሮ ቡታን፣ ኬፕ ቨርዲ፣ ዶሚኒካ፣ ጋና፣ ላኦስ፣ ሞሪታኒያ፣ ሞንጐሊያ፣ ሞዛምቢክ፣ ሣሞኣ፣ ሣኦቶሜ ፕሪንቼቤ፣ ሴኔጋል፣ ታንዛኒያ እና ኡጋንዳ ናቸው፡፡ በሌላ በኩል 24 የአለም ሀገሮች የውጭ እዳቸው በሚያሰጋ ደረጃ እየጨመረና ወደ አደጋው ቀጠናም እየተንደረደሩ ነው በሚል ተጠቅሰዋል፡፡
አንዳንድ በአስጊ ደረጃ እዳ ውስጥ ተዘፍቀዋል የተባሉ ሀገራት፣ የተበደሩትን ገንዘብ ለተገቢው
አላማ መጠቀም አለመቻላቸው ለቀውስ እንደዳረጋቸው በሪፖርቱ የተጠቆመ ሲሆን በዚህ ረገድ ጋና ምሣሌነት ተጠቅሳለች፡፡ ሌሎችም አዋጭ የሆነ የብድር አመላለስ ስርአት ባለመከተላቸው የችግሩ ሠለባ እየሆኑ እንደመጡ የጠቆመው ሪፖርቱ፤ እነዚህ ሀገራት ከዚህ እዳ የሚወጡበትን መንገድ ካላጤኑ ከፍተኛ ቀውስ ሊገጥማቸው ይችላል ብሏል፡፡ በአለም አቀፍ ደረጃ የግል ኩባንያዎችና መንግስታት አለም ባንክን ከመሳሰሉ አበዳሪ ተቋማት ከ2009 እ.ኤ.አ ጀምሮ በየአመቱ የሚበደሩት ገንዘብ በከፍተኛ ደረጃ እየጨመረ ነው ተብሏል፡፡ በ2013 እ.ኤ.አ የአለም ሀገራት አጠቃላይ የብድር መጠን 11.3 ትሪሊዮን ዶላር ሲሆን በ2014 13.8 እንዲሁም በዘንድሮው አመት 14.7 ትሪሊዮን ዶላር መሆኑን ሪፖርቱ አመልክቷል፡፡ 

    ተቃዋሚ ፓርቲዎች ከግንቦቱ ምርጫ በኋላ አባሎቻቸውና ደጋፊዎቻቸው ላይ ግድያ፣ እስራትና እንግልት እየተፈፀመባቸው መሆኑን የገለፁ ሲሆን መድረክ 5 አባሎቹ እንደተገደሉበት ስታውቋል። ሰማያዊ ፓርቲም በአባላቱ ላይ እየተፈፀመ ነው ያለው ግድያ፣ እስርና እንግልት በአስቸኳይ እንዲቆም ሰሞኑን ጠይቋል፡፡ ድረክ በሰጠው በመግለጫ፤ በደቡብና በኦሮሚያ ክልሎች በአባላቱ ላይ የሚፈፀሙት እስራቶችና
ንግልቶች ተጠናክረው እንደቀጠሉ አመልክቷል፡፡ ከምርጫው በኋላ በትግራይ፣ በኦሮሚያ እና ቡብ ክልል ከተገደሉት 4 የመድረክ አባላት በተጨማሪ ሰኔ 27 ቀን በደቡብ ክልል በከፋ ዞን፣ ቢግንቦ ወረዳ፣ በኢዲዩ ካካ የምርጫ ክልል፣ በጎጀብ ምርጫ ጣቢያ የመድረክ ታዛቢ የነበሩት አቶ አስራት ኃይሌ ማንነታቸው ባልታወቁ ሰዎች ግድያ እንደተፈፀመባቸው መድረኩ ለአዲስ አድማስ በላከው መግለጫ አመልክቷል፡፡
የሟቹ አስከሬን ከቀብር ቦታ ጋር በተያያዘም ከፍተኛ እንግልት አጋጥሞት እንደነበር የጠቀሰው መድረክ፤  እስከ ሐምሌ 1 ቆይቶ በህብረተሰቡ ትብብር የቀብር ስነ-ስርአቱ ሊፈፀም መቻሉን አስታውቋል፡፡ በተለያዩ የደቡብና የኦሮሚያ ዞኖችና ወረዳዎች በምርጫው የመድረክ ታዛቢ ወኪሎች የነበሩ፣ አባላት እና ደጋፊዎች ከፓርቲው ጎን በመቆማቸው ብቻ የተለያዩ ማህበራዊ አገልግሎቶች እንዳያገኙ ከመደረጉም በላይ ከፓርቲው አባልነት ራሳቸውን እንዲያገሉ ግፊት እየተደረገባቸው ነው ብሏል - መድረክ፡፡
ከዚሁ ጋር በተያያዘ ሰማያዊ ፓርቲ፤ “የወለደውን የረሳ ብሶት የወለደው ስርአት! የዘመቻ እስርና ግድያ ተጠናክሮ ቀጥሏል፡፡” በሚል ሰሞኑን በፅ/ቤቱ በሰጠው መግለጫ፤ በግንቦቱ ምርጫ ማግስት በምርጫው በንቃት ይሳተፉ የነበሩ ዜጎች እየታደኑ እየታሰሩ ነው ብሏል፡፡ ፓርቲው፤ ዜጎችን በፖለቲካ አመለከታቸው ሳቢያ ከስራ ማፈናቀል፣ ማሰር፣ ማሸማቀቅና ማንገላታት እንዲቆም አበክሮ ጠይቋል።
“በሰላማዊ መንገድ የሚታገሉ የሰማያዊ፣ የመኢአድ፣ የቀድሞ አንድነት፣ የመድረኩና ሌሎችም የፖለቲካ ፓርቲ አባላት ኢላማ ተደርገው እየተሳደዱና በጅምላ እየታሰሩ እንዲሁም በአሰቃቂ ሁኔታ እየተገደሉ ይገኛሉ” ብሏል - ፓርቲው በመግለጫው፡፡ ከምርጫው ማግስት ጀምሮ በተቃዋሚ ፓርቲ አባላት ላይ እየደረሰ ነው ያለው ግድያ፣ እስርና እንግልትም በአስቸኳይ እንዲቆም ሰማያዊ ፓርቲ ጠይቋል፡፡