Administrator

Administrator

ሩስያ መጠነ ሰፊ ወረራ ልታደርግብን ትችላለች ብለዋል

   በሩስያ በሚደገፉት የዩክሬን አማጽያን እና በመንግስት ጦር መካከል ባለፈው ረቡዕ የከፋ ግጭት መከሰቱን ተከትሎ፣ ፕሬዚደንት ፔትሮ ፖሮሼንኮ የጦር ሃይላቸው ከሩስያ ሊቃጣ ከሚችል የተደራጀ መጠነ ሰፊ ወረራ አገሪቱን ለመከላከል በተጠንቀቅ እንዲቆም ማሳሰባቸውን ሮይተርስ ዘገበ።
የሩስያ ወታደሮች ከዩክሬን አማጽያን ጋር በመተባበር በምስራቃዊ የአገሪቱ ክፍል ጥቃት እየፈጸሙ ነው ሲሉ ከትናንት በስቲያ ለአገሪቱ የፓርላማ አባላት የተናገሩት ፕሬዚዳንቱ፣ ጦራቸው ከአማጽያኑ የሚቃጣበትን ጥቃትና ከሩስያ ጋር በሚያዋስኗት ሁሉም የድንበር አካባቢዎች ሊፈጸምበት ከሚችለው ሰፊ ወረራ አገሪቱን ለመከላከል በበቂ ሁኔታ መዘጋጀት ይኖርበታል ብለዋል፡፡
የዩክሬን አማጽያን ባለፈው ረቡዕ ማሪንካ ከተማን ለመቆጣጠር ባደረጉት ሙከራ፣ ከመንግስት ጦር ጋር በከባድ የጦር መሳሪያዎች የታገዘ አስከፊ ግጭት መደረጉን የጠቆመው ዘገባው፣ ፕሬዚዳንቱም ግጭቱ ሩስያና አማጽያኑ በአገሪቱ ላይ ቀጣይ የተደራጀ ወታደራዊ ጥቃት እንደሚሰነዘር የሚያሳይ ነው ማለታቸውን ገልጧል፡፡
ዩክሬንና የኔቶ አባል አገራት የሆኑ አጋሮቿ፣ በአገሪቱ ምስራቃዊ አካባቢዎች የሚገኙ ሁለት ግዛቶችን ከፊል አካባቢዎች ይዘው ለሚገኙት አማጽያን የጦር መሳሪያዎችንና ወታደሮችን በመላክ ጥቃት እየፈጸመች ነው ሲሉ ሩስያን በተደጋጋሚ ሲከሱ መቆየታቸውን የጠቆመው ዘገባው፣ ባለፈው የካቲት ወር ላይ የተኩስ አቁም ስምምነት ቢደረስም፣ መጠነኛ ግጭቶች ሲከሰቱ መቆየታቸውንና፣ ባለፈው ረቡዕም አስከፊ የተባለው ግጭት መከሰቱን ገልጧል፡፡ ምዕራባውያን አገራት ሩስያ በሰላም ስምምነቱ ውስጥ የተካተቱ ሃላፊነቶቿን አልተወጣችም ሲሉ የተቹ ሲሆን፣ ወታደሮቿን ከዩክሬን ግዛት ማስወጣትና ለአማጽያኑ የጦር መሳሪያ ድጋፍ ማድረጓን ማቆም አለባት ማለታቸውን ዘገባው አስረድቷል፡፡
ሩስያ በበኩሏ፤ ግጭቱን እንደገና የቆሰቆሰችው ዩክሬን ናት፣ ይህንንም ያደረገችው በቅርቡ በሩስያ ላይ የኢኮኖሚ ማዕቀብ ይጣል አይጣል የሚለውን ይወስናል ተብሎ በሚጠበቀው የአውሮፓ ህብረት ላይ ጫና ለማሳደር በማሰብ ነው ብላለች፡፡
ፕሬዚዳንት ፖሮሼንኮ በአሁኑ ወቅት 9ሺህ ያህል የሩስያ ወታደሮች ድንበር ጥሰው ገብተው በግዛታችን ወታደራዊ እንቅስቃሴ እያደረጉ ነው ቢሉም፣ ሩስያ በበኩሏ መሰረተቢስ ውንጀላ ነው ስትል የፕሬዚዳንቱን ንግግር ማጣጣሏን ዘገባው ጠቁሟል፡፡
በአሁኑ ወቅት ከአጠቃላይ አገራዊ ምርቷ 5 በመቶውን ለወታደራዊ በጀት የመደበችው ዩክሬን፣ በቀጣዩ አመትም በወታደራዊ በጀቷ ላይ ጭማሪ ልታደርግ እንደምትችል ፕሬዚዳንት ፖሮሼንኮ ለፓርላማ አባላቱ ባደረጉት ንግግር መግለጻቸውንም ዘገባው አክሎ ገልጧል፡፡

የብሩንዲው ፕሬዚዳንት ፔሪ ንኩሩንዚዛ ህገመንግስቱ ከሚፈቅድላቸው ውጪ ለሶስተኛ ዙር በምርጫ ለመወዳደር መወሰናቸውን ተከትሎ በአገሪቱ የተቀሰቀሰው ግጭት በዚህ ሳምንትም ያገረሸበት ሲሆን  የአገሪቱ የፓርላማና ፕሬዚዳንታዊ ምርጫ ለሶስተኛ ጊዜ ዳግም መራዘሙን ቢቢሲ ዘገበ፡፡ በአገሪቱ ያለው ሁኔታ ሰላማዊ ምርጫን ለማከናወን አያስችልም በሚል ምርጫውን እንዲያራዝሙ ከአፍሪካውያንና ምእራባውያን መንግስታት ጫና ሲደረግባቸው የቆዩት ፕሬዚዳንቱ፣ ምርጫው እንዲራዘምና በመጪው ነሃሴ ወር መጨረሻ እንዲካሄድ መወሰናቸውን ከትናንት በስቲያ አስታውቀዋል፡፡
ከአገሪቱ ዋነኛ የተቃዋሚ ፓርቲ መሪዎች አንዱ የሆኑት አጋቶን ሩዋሳ ከቢቢሲ ጋር ባደረጉት ቃለ መጠይቅ፣ ፕሬዚዳንት ንኩሩንዚዛ አምባገነን መሪ ስለሆኑ ከስልጣናቸው መውረድ አለባቸው ያሉ ሲሆን፣ የጸጥታ ሁኔታው ሳይሻሻል፣ ገለልተኛ የምርጫ ኮሚሽን ሳይመረጥና የግል ሚዲያው ላይ የሚደረገው ጫና ሳያበቃ በአገሪቱ ምርጫ ሊከናወን አይችልም ብለዋል፡፡ የብሩንዲ ምርጫ ከዚህ ቀደም እንዲራዘም በተወሰነው መሰረት፣ የፓርላማ ምርጫው ትናንት፣ የፕሬዚዳንታዊ ምርጫው ደግሞ በሰኔ ወር መጨረሻ ሊካሄድ ቀን ተቆርጦ ነበር፡፡
ፕሬዚዳንቱ በምርጫ ለመወዳደር መወሰናቸውን ማስታወቃቸውን ተከትሎ ያልተሳካ መፈንቅለ መንግስት መካሄዱና በአገሪቱ በተቀሰቀሰው ግጭት ከ20 በላይ ዜጎች መሞታቸውን፣ በመቶ ሺህዎች የሚቆጠሩ ብሩንዲያውያንም ወደ ጎረቤት አገራት መሰደዳቸውን ባለፈው ሳምንት መዘገባችን ይታወሳል፡፡

የብሩንዲው ፕሬዚዳንት ፔሪ ንኩሩንዚዛ ህገመንግስቱ ከሚፈቅድላቸው ውጪ ለሶስተኛ ዙር በምርጫ ለመወዳደር መወሰናቸውን ተከትሎ በአገሪቱ የተቀሰቀሰው ግጭት በዚህ ሳምንትም ያገረሸበት ሲሆን  የአገሪቱ የፓርላማና ፕሬዚዳንታዊ ምርጫ ለሶስተኛ ጊዜ ዳግም መራዘሙን ቢቢሲ ዘገበ፡፡ በአገሪቱ ያለው ሁኔታ ሰላማዊ ምርጫን ለማከናወን አያስችልም በሚል ምርጫውን እንዲያራዝሙ ከአፍሪካውያንና ምእራባውያን መንግስታት ጫና ሲደረግባቸው የቆዩት ፕሬዚዳንቱ፣ ምርጫው እንዲራዘምና በመጪው ነሃሴ ወር መጨረሻ እንዲካሄድ መወሰናቸውን ከትናንት በስቲያ አስታውቀዋል፡፡
ከአገሪቱ ዋነኛ የተቃዋሚ ፓርቲ መሪዎች አንዱ የሆኑት አጋቶን ሩዋሳ ከቢቢሲ ጋር ባደረጉት ቃለ መጠይቅ፣ ፕሬዚዳንት ንኩሩንዚዛ አምባገነን መሪ ስለሆኑ ከስልጣናቸው መውረድ አለባቸው ያሉ ሲሆን፣ የጸጥታ ሁኔታው ሳይሻሻል፣ ገለልተኛ የምርጫ ኮሚሽን ሳይመረጥና የግል ሚዲያው ላይ የሚደረገው ጫና ሳያበቃ በአገሪቱ ምርጫ ሊከናወን አይችልም ብለዋል፡፡ የብሩንዲ ምርጫ ከዚህ ቀደም እንዲራዘም በተወሰነው መሰረት፣ የፓርላማ ምርጫው ትናንት፣ የፕሬዚዳንታዊ ምርጫው ደግሞ በሰኔ ወር መጨረሻ ሊካሄድ ቀን ተቆርጦ ነበር፡፡
ፕሬዚዳንቱ በምርጫ ለመወዳደር መወሰናቸውን ማስታወቃቸውን ተከትሎ ያልተሳካ መፈንቅለ መንግስት መካሄዱና በአገሪቱ በተቀሰቀሰው ግጭት ከ20 በላይ ዜጎች መሞታቸውን፣ በመቶ ሺህዎች የሚቆጠሩ ብሩንዲያውያንም ወደ ጎረቤት አገራት መሰደዳቸውን ባለፈው ሳምንት መዘገባችን ይታወሳል፡፡

 አሸናፊው ሮቦት 3.5 ሚሊዮን ዶላር ይሸለማል

    በሮቦቲክስ መስክ የተሰማሩ 24 የአለማችን ኩባንያዎችና የምርምር ቡድኖች ያመረቷቸው ሮቦቶች የተሳተፉበትና 3.5 ሚሊዮን ዶላር ሽልማት የሚያስገኘው የዳርፓ የሮቦቶች ውድድር ትናንትና ዛሬ በአሜሪካ እየተካሄደ እንደሚገኝ ቢቢሲ ዘገበ፡፡
በአሜሪካው መከላከያ ቢሮ ፔንታጎን ድጋፍ በሎሳንጀለስ አቅራቢያ በመከናወን ላይ በሚገኘው በዚህ ውድድር የሚሳተፉ ሮቦቶች አደጋን የመቋቋም ብቃታቸውን የሚያሳዩ አስቸጋሪ ተግባራትን እንዲፈጽሙ በማድረግ አሸናፊው ይለያል ተብሏል፡፡
ሮቦቶቹ እንዲያከናውኗቸው ከተመደቡላቸው ስምንት ተግባራት መካከል፡- መኪና መንዳት፣ በር መክፈትና ማለፍ፣ ግድግዳ መብሳት፣ በደረጃዎች ላይ መወጣጣት የሚገኙበት ሲሆን፣ በውድድሩ ላይ የሚገለጽ ሌላ ለየት ያለ ተልዕኮም እንዲፈጽሙ ይደረጋል፡፡
እያንዳንዱ ሮቦት እነዚህን ስምንት ተግባራት ለማከናወን ሁለት ሙከራዎች የሚሰጡት ሲሆን ፈጥኖ ተግባራቱን በተሳካ ሁኔታ ማከናወንም ለአሸናፊነት በመስፈርትነት ከተቀመጡት ነጥቦች አንዱ እንደሆነ ዘገባው ጠቁሟል፡፡
የውድድሩ አዘጋጅ የሆኑት ዶክተር ጊል ፕራት እንዳሉት፣ የዘንድሮው ውድድር ከአምናው ጋር ሲነጻጸር በአስር እጥፍ አስቸጋሪ ይሆናል ተብሎ ይጠበቃል፡፡
የተለያዩ የአለም አገራት የሮቦቲክስ ዘርፍ ኩባንያዎችና የምርምር ቡድኖች ለውድድሩ የቀረቡ ቢሆንም፣ የመጀመሪያውን ማጣሪያ አልፈው ለፍጻሜ የደረሱት፣ 24 መሆናቸውንና ከእነዚህም መካከል የአሜሪካ፣ የደቡብ ኮርያ፣ የጃፓን፣ የጀርመንና የጣሊያን ኩባንያዎች እንደሚገኙበት ዘገባው አመልክቷል፡፡  

  ከአለማችን ታላላቅ የኤሌክትሮኒክስ እቃዎች አምራች ኩባንያዎች ተርታ የሚሰለፈው የጃፓኑ ሻርፕ ኩባንያ፣ በያዝነው የፈረንጆች አመት  ብቻ 1.45 ቢሊዮን ዶላር ይከስራል ተብሎ እንደሚጠበቅ ሮይተርስ ዘገበ፡፡
ከቅርብ አመታት ወዲህ እየደረሰበት ካለው ኪሳራ ለማገገም ደፋ ቀና ማለቱን የቀጠለው ሻርፕ፣ በዘንድሮው አመት  1.45 ቢሊዮን ዶላር ኪሳራ ይደርስበታል ተብሎ እንደሚጠበቅ የጃፓኑ ኮዮዶ ኒውስ ይፋ ያደረገውን መረጃ ጠቅሶ ዘገባው ገልጧል፡፡
ኩባንያው ባለፈው አመት 222 ቢሊዮን የጃፓን የን መክሰሩን ያስታወሰው ዘገባው፣ የአምናው ኪሳራው ባለፉት አራት አመታት ከደረሱበት ኪሳራዎች በሶስተኛ ደረጃ ላይ እንደሚገኝም ገልጧል፡፡ ኩባንያው ባለፉት አመታት ለከፍተኛ ኪሳራ የተዳረገው በተለያዩ አለማቀፋዊና ውስጣዊ ምክንያቶች መሆኑን የጠቆመው ዘገባው፣ ከእነዚህም መካከል የምርቶች ሽያጩ መቀነሱ፣ የገበያ ውድድሩ ከፍተኛ መሆኑና የወጪዎች መብዛት ይጠቀሳሉ ብሏል፡፡ ሻርፕ ባለፈው አመት በአለም ዙሪያ ከሚገኙ 49 ሺህ ሰራተኞቹ መካከል 10 በመቶውን ከስራ እንደቀነሰና ከእነዚህም መካከል 3ሺህ 500 የሚሆኑት በጃፓን ይሰሩ የነበሩ መሆናቸውንም ዘገባው አክሎ ገልጧል፡፡

የማይመለሱ 4 ነገሮች፡- ከአፍ የወጣ ቃል፣ የተወረወረ ቀስት፣ ያለፈ ህይወት እና የባከነ ዕድል፡፡
የቻይናውያን አባባል
ለማቀድ መስነፍ ለመውደቅ ማቀድ ነው፡፡
የቻይናውያን አባባል
ማለም ብቻ በቂ አይደለም፤ መምታት አለብህ፡፡
የጣሊያኖች አባባል
መሬት ላይ እሾህ ከበተንክ ባዶ እግርህን አትሂድ፡፡
የጣሊያኖች አባባል
ሁልጊዜ የምትሰጥ ከሆነ ሁልጊዜ ይኖርሃል፡፡
የቻይናውያን አባባል
በአንድ እጅህ ሁለት እንቁራሪቶችን ለመያዝ አትሞክር፡፡
የቻይናውያን አባባል
የተጠበሰች ዳክዬ መብረር አትችልም፡፡
የቻይናውያን አባባል
አበቦች በያዛቸው እጅ ላይ መዓዛቸውን ይተዋሉ፡፡
የቻይናውያን አባባል
ጠብ ከፈለግህ ለጓደኛህ ገንዘብ አበድረው፡፡
የቻይናውያን አባባል
የምላስ ብዕር፣ የልብ ቀለም ውስጥ መነከር አለበት፡፡
የቻይናውያን አባባል
የአንድ ዓመት ብልጽግና ከፈለግህ እህል ዝራ፤ የ10 ዓመት ብልጽግና ከፈለግህ ዛፎች ትከል፤ የ100 ዓመት ብልጽግና ከፈለግህ ሰዎችን አልማ፡፡
የቻይናው ያን አባባል
የአንድ ሰዓት ደስታ ከፈለግህ አሸልብ፤ የአንድ ቀን ደስታ ከፈለግህ ሃብት ውረስ፤ የዕድሜ ልክ ደስታ ከፈለግህ ሰዎችን እርዳ፡፡
የቻይናውያን አባባል

ወይዘሮ ተናኘ ስዩም “የፍቅር ድንግልና” በሚል ርዕስ ፅፈው ያሳተሙት ረጅም ልብወለድ መፅሃፍ በዛሬው ዕለት ከጠዋቱ 2፡30 ጀምሮ በአምስት ኪሎ ድህረ ምረቃ አዳራሽ ይመረቃል፡፡ በምረቃ ስነ - ስርዓቱ ላይ ደራሲ አበረ አዳሙ በመፅሃፉ ላይ ሥነ - ፅሁፋዊ ዳሰሳ ያቀርባል ተብሏል፡፡
ደራሲዋ የዕውቋ ድምፃዊት ጂጂ (እጅጋየሁ ሽባባው) እናት እንደሆኑ ታውቋል፡፡ የልቦለዱ ታሪክ ከኢጣሊያ ወረራ በፊትና በኋላ የነበረች አንዲት ወጣት ላይ የሚያጠነጥን ሲሆን የወቅቱን ባህላዊና ማህበራዊ ገፅታ ያሳያል። በ349 ገፆች የተቀነበበው “የፍቅር ድንግልና”፤ በ100 ብር ለገበያ ቀርቧል፡፡ 

የወጣት ፍሬዘር ዘውዴን (ቬኛ) የግጥሞችና ደብዳቤዎች ስብስብ የያዘው “የፍቅር ገፆች” የተሰኘ መድበል ካለፈው ሳምንት ጀምሮ ለንባብ በቅቷል፡፡
መፅሃፉ በ110 ገፆች 52 ግጥሞችንና 12 ደብዳቤዎችን ያካተተ ሲሆን ለአገር ውስጥ በ30 ብር፣ ለውጭ አገራት በ9.99 ዶላር እንደሚሸጥ ታውቋል፡፡

በአለማየሁ ገበየሁ የተፃፈው  “የረከሰ ፍርድ በኢትዮጵያ” የተሰኘ የአጫጭር ወጐች መፅሐፍ ለንባብ በቃ፡፡
ጭብጡን ፖለቲካዊና ማህበራዊ ጉዳዮች ላይ ያደረገው መጽሐፉ፤ ታሪኮቹ በወግ መልክ  የቀረቡ ናቸው፡፡ ደራሲ አለማየሁ ገበየሁ የኢትዮጵያ ፕሬስ ድርጅትን ጨምሮ በተለያዩ ሚዲያዎች በጋዜጠኝነት መስራቱ ታውቋል፡፡
ደራሲው በእለት ማስታወሻ ደብተሩ የመዘገባቸውን አስገራሚ ሁነቶች በወግ መልክ ማቅረቡን  የጠቆመ ሲሆን መፅሃፉ በ49 ብር ለገበያ ቀርቧል፡፡

 ባለፈው ዓመት በአገራችን ለመጀመሪያ ጊዜ በብሔራዊ ቴአትር የተከበረው “የዓለም የቴአትር ቀን”፤ በደሴ ከተማና በኮምበልቻ እንደሚከበር በባህልና ቱሪዝም ሚ/ር የኢትዮጵያ ብሔራዊ ቴአትር አስታወቀ፡፡
“ቴአትር ለማህበራዊ ለውጥ፤ ማህበራዊ ለውጥ ለቴአትር” በሚል መሪ ቃል ከዛሬ ጀምሮ ለ3 ቀናት የሚከበረውን በዓል ወሎ ዩኒቨርሲቲና የባህልና ትብብር ዳይሬክቶሬት በጋራ እንዳዘጋጁት ታውቋል፡፡
“የዓለም የቴአትር ቀን” በደሴና ኮምበልቻ በተለያዩ አዳራሾች እንደሚከበር የጠቆሙት አዘጋጆቹ፤ በየመድረኩ ቴአትሮች፣ ትውፊታዊ ድራማዎች፣ ልዩ የሙዚቃ ዝግጅቶችና ቱባ ባህልን የሚያንፀባርቁ ውዝዋዜዎች፣ የቅኔ ጉባኤ፣ መንዙማና ሌሎች ኪነ - ጥበባት ይቀርባሉ ብለዋል፡፡
“የዓለም የቴአትር ቀን” ከ1962 ዓ.ም አንስቶ በዓለም አቀፍ ደረጃ መከበር የጀመረ ሲሆን ዘንድሮ ለ53ኛ ጊዜ እንደተከበረ ተጠቁሟል፡፡