Administrator

Administrator

  ከ1.5 ሚ. ብር በላይ ፈጅቷል

   የጠፈር ሳይንስ ተመራማሪ የነበሩትን የሳይንቲስት ዶ/ር ቅጣው እጅጉ ህይወት የሚዳስስ የ50 ደቂቃ ዘጋቢ ፊልም በዛሬው ዕለት ከምሽቱ 12፡30 ጀምሮ በሂልተን ሆቴል ይመረቃል፡፡
“ልጃችን” የተሰኘውንና ከ1.5 ሚ. ብር በላይ ወጪ የተደረገበትን ይሄን ዘጋቢ ፊልም ሰርቶ ለማጠናቀቅ ከ2 ዓመት በላይ እንደፈጀ የዶ/ር ቅጣው እጅጉ ቤተሰቦች ጠቁመዋል፡፡ ከቦንጋ እስከ አሜሪካ ድረስ ያለውን የሳይንቲስቱን ህይወት በስፋት ይዳስሳል በተባለለት በዚህ ዘጋቢ ፊልም፤ ከዶ/ር ቅጣው ጋር ተያይዘው የሚነሱ በርካታ የተዛቡ ጉዳዮች ምላሽ ተሰጥቶባቸዋል ተብሏል፡፡

የደራሲ ተስፋዬ ዘርፉ “የስደታችን ማስታወሻ” የተሰኘው መፅሃፍ በነገው ዕለት ከቀኑ 8 ሰዓት ጀምሮ ውይይት እንደሚካሄድበት ሚዩዚክ ሜይዴይ ኢትዮጵያ ገለፀ፡፡ ለውይይቱ መነሻ ሀሳብ የሚያቀርቡት በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ የፕሬስ ኤዲተር የሆኑት አቶ ብርሃኑ ደቦጭ ሲሆኑ ውይይቱ በብሔራዊ ቤተ - መፃህፍትና ቤተ - መዛግብት ኤጀንሲ አዳራሽ እንደሚካሄድ ታውቋል፡፡ የሥነ - ፅሑፍ አፍቃሪያን በውይይቱ ላይ እንዲገኙ ሚዩዚክ ሜይዴይ ጥሪ ጋብዟል፡፡

Saturday, 06 June 2015 14:21

የፍቅር ጥግ

ፍቅር የሚያንዘፈዝፍ ደስታ ነው፡፡
ካህሊል ጂብራን
እግዚአብሄር የተሰበረ ልብ መጠገን ይችላል፡፡ ነገር ግን ስብርባሪዎቹን ሁሉ ማግኘት አለበት፡፡
ያልታወቀ ደራሲ
የትዳር ግብ ተመሳሳይ ነገር ማሰብ ሳይሆን አብሮ ማሰብ ነው፡፡
ሮበርት ሲ.ዶድስ
ሚስት ጥሩ ባል ሲኖራት ፊቷ ላይ ያስታውቃል፡፡
ገተ
አባት ለልጆቹ ማድረግ የሚችለው ትልቁ ነገር እናታቸውን መውደድ ነው፡፡
ቲዎዶር ሄስበርግ
አንዳንዴ አንድ ሰው ስናጣ መላው ዓለም ህዝብ አልባ የሆነ ይመስለናል፡፡
ላማርቲን
እግዚአብሔር የተሰበረ ልብ ላላቸው ቅርብ ነው፡፡
የአይሁዶች አባባል
ሁልጊዜ ከሚስቴ ጋር እጅ ለእጅ እንያያዛለን። ከለቀቅኋት አንድ ነገር ትገበያለች፡፡
ሄኒ ያንግማን
አብሮ መሆን ጅማሮ ነው፡፡ አብሮ መቀጠል ዕድገት ነው፡፡ አብሮ መስራት ስኬት ነው፡፡
ሔነሪ ፎርድ
በእኔ ቤት ውስጥ አለቃው እኔ ነኝ፤ የሚስቴ ሚና የውሳኔ ሰጪነት ብቻ ነው፡፡
ውዲ አለን
ትዳር ለማደግ የመጨረሻችን ምርጥ አጋጣሚ ነው፡፡
ጆሴፍ ባርዝ
ሃዘን በጊዜ ክንፍ በርሮ ይሄዳል፡፡
ዣን ዲ ላፎንቴን
አንተ በልቤ ክንፍ በርረህ ሄድክ፣ እኔን ግን ክንፍ አልባ አደረግኸኝ፡፡
ቴሪ ጉይሌሜትስ
ትዳርን ጠብቆ የሚያቆየው ሰንሰለት አይደለም፡፡ ክሮች ናቸው፡፡ ሰዎችን በአንድ ላይ ሰፍተው የሚያቆዩት በመቶዎች የሚቆጠሩ ቀጫጭን ክሮች ናቸው፡፡
ሳይሞን ሲኞሬት

Saturday, 06 June 2015 14:06

የፀሐፍት ጥግ

 አገር ተራኪዎቿን ካጣች ልጅነቷን ታጣለች፡፡
ፒተር ሃንድኬ
ከእንቅልፍ ማንቂያ ደወል ሰዓት አልፈልግም፡፡ ሃሳቦቼ ይቀሰቅሱኛል፡፡
ሬይ ብራድበሪ ደብሊው ዲ
ጥሩ የመሰለህን ነገር ለኋለኛው የመጽሐፍህ ክፍል ወይም ለሌላ መጽሐፍህ አታስቀምጠው፡፡ ሁሉንም ነገር አሁን አውጣው፡፡
አኒ ዲላርድ
ሁልጊዜ መፃፍ የምጀምረው በንፁህ ወረቀትና በቆሸሸ አዕምሮ ነው፡፡
ፓትሪክ ዴኒስ
ፀሐፍት የሚኖሩት ሁለት ጊዜ ነው፡፡
ናታሊ ጐልድበርግ
ወረቀትህን በልብህ እስትንፋሶች ሙላው፡፡
ዊሊያም ዎርድስዎርዝ
ሙሴ ዛሬ በህይወት ቢኖር ኖሮ፣ አስርቱን ትዕዛዛት ከተራራ ላይ ይዞ ይወርድና ለሚቀጥሉት አምስት ዓመታት ለማሳተም መከራውን ይበላ ነበር፡፡
ያልታወቀ ደራሲ
ፀሐፊዎች የአኗኗር ዘይቤ የላቸውም፡፡ በትንሽ ክፍል ውስጥ ተቀምጠው መፃፍ ብቻ ነው፡፡
ኖርማን ሜይለር
አንድ የሆነ ሰው ካላበሸቅህ መፃፍህ ትርጉም የለውም፡፡
ኪንግስሌይ አሚስ
ጥሩ ሂስ የሚፃፍልኝ ራሴን ካጠፋሁ ብቻ ነው፡፡
ኢድዋርድ አልቢ
መጥፎ ሂስ ቁርስህን ሊያበላሽብህ ይችላል፤ ምሳህን እንዲያበላሽብህ ግን ልትፈቅድለት አይገባም፡፡
ኪንግስሌይ አሚስ
ሥነፅሁፍ ሁሉ ሃሜት ነው፡፡
ትሩማን ካፖቴ
አንድ ቀን ለመሰረቅ የሚበቃ ነገር እንደምፅፍ ተስፋ አደርጋለሁ፡፡
ያልታወቀ ደራሲ
መፃፍ ቀላል ነው፡፡ ቁጭ ብለህ የደም ስርህን መክፈት ብቻ ነው፡፡
ሬድ ባርበር
ለፃፍከው ነገር ጥብቅና መቆም በህይወት የመኖርህ ምልክት ነው፡፡
ዊሊያም ዚንሰር ደብሊው ዲ

  ከዕለታት አንድ ቀን ቹዌንጌር የሚባል አንድ የቺን ልዑል ነበረ፡፡ ይህ ልዑል ቀን ጐሎበት ወደሌላ ቼንግ ወደሚባል አገር ተሰደደ፡፡ ወደ አገሩ እስኪመለስም በድህነት፤
“ካገሩ የወጣ አገሩ እስኪመለስ
ቢጭኑት አህያ ቢለጉሙት ፈረስ”
እያለ በቻይኒኛ አሳዛኝ ህይወቱን ይመራ ጀመር፡፡
አንድ ቀን በተሰደደበት አገር በቼንግ ቤተመንግሥት አጠገብ ሲያልፍ ድንገት ንጉሡ ሲወጣ ይደርሳል፡፡ ንጉሡ የዚህን ልዑል ማንነት ሳያውቅ፤
“የማን ነው ቡቱቷም! እንደነዚህ ዓይነት ሰዎች በመንገድ ላይ እንዳላይ አላልኩም?! ይሄን ጭርንቁሳም ከመንገዴ አስወግዱልኝ!” አለ፡፡
የንጉሡ ባለሟል ግን ሰውዬው ማን እንደሆነ ስለገባው፤
“ንጉሥ ሆይ! ይሄ ሰው ጊዜ ጥሎት ነው እንጂ የተከበረ ልዑል ነበር፡፡ በታላቅ አክብሮት ብንይዘው ጥሩ ይመስለኛል፡፡ ደህና ቦታ አስቀምጠንም በዐይነ - ቁራኛ ብናየው ይሻላል!” አለ፡፡
ንጉሡ ግን የዚያን ሰው ጉስቁልናና ጨብራራ ፀጉር ብቻ ነበርና የተመለከተው የቧለሟሉን ምክር ከመጤፍ ሳይቆጥር ልዑሉን ክፉኛ ሰደበው፡፡
ባለሟሉም፤ እንደገና፤
“ንጉሥ ሆይ! ግርማዊነትዎ በአክብሮት ሊይዘው ካልቻለ፣ ነገ የሚመጣውን ማናቸውንም ነገር ከወዲሁ ለመቅጨት ወይ ይሄን ሰው ማስወገድ ይኖርብዎታል!” አለና አስጠነቀቀ፡፡
ንጉሡ ግን፤
“በእንደዚህ ያለ ቆሻሻ ላይ እጄን አላሳርፍም!” ብሎ አንቋሾት ሄደ፡፡ ከጊዜ በኋላ ልዑል ወደ አገሩ ተመለሰ፡፡
ሁኔታዎች ሁሉ ተለዋወጡ፡፡ ያ ልዑል ማ ደግ እንደሆነለት፣ ማ ክፉ እንደሠራበት ያውቃል፡፡ ከሰው ሁሉ ግን ያንን ንጉሥ አልረሳውም፡፡ ስለሆነም ጦሩን ሁሉ አደራጅቶ ወደ ቼንግ ዘመተ፡፡ ስምንት ግዛቶች ያዘ፡፡ ግዛተ - መንግሥቱን አፈራረሰ፡፡ የቼንግን ንጉሥም ወደራሱ ወደ ልዑሉ አገር እንዲሰደድ አደረገ፡፡
*   *   *
ሰው ነገ ምን እንደሚሆን አይታወቅም፡፡ ዛሬ ምናምኒት አቅም የሌለው ሰው፣ ወደፊት ትልቅ ሥልጣን ያለው ሰው ሊሆን ይችላል፡፡ በህይወታችን ብዙ ነገር ልንሸከም፣ ልንረሳም እንችላለን፡፡ መናቅና መሰደብን ግን አንረሳም፡፡ ቅስም የሚያም ነገር በቶሎ ከልባችን አይወጣም፡፡ ፈረንጆች “ረዥም የማስታወስ ችሎታ ካለው እባብ ጋር አትጣላ” ይላሉ፡፡ አላስፈላጊ የሆነ ሌሎችን የማጐሳቆል ተግባር ጥቅም የለውም፡፡ ሌላው ሰው፤ ጊዜ የገፋው አንሶ እኛ ተጨምረን “የወደቀ ዛፍ ምሣር ይበዛበታል” የሚለውን ብናስዘምር የማታ ማታ፤ ለጊዜያዊ እርካታ ብለን አሁን የፈፀምነው ኋላ መዘዙ ብዙ ሆኖ እናገኘዋለን፡፡ ዓለምን በተለይም አገራችንን የቂም ቀለበት መሽከርከሪያ ምህዋር አናድርጋት፡፡ አርቀን እናስብ፡፡ ሼክስፒር በሐምሌቱ፤ በፀጋዬ ገ/መድህን ብዕር ልሣን፤
“ዛሬ ለወግ ያደረግሺው፣ ወይ ለነገ ይለምድብሻል
ልማድ ፊት እንዳሳዩት ነው፣ ወይ ይጠፋል ወይ ያጠፋል”…ይለናል፡፡ እንደወግ የምናደርገውን ነገር ሁሉ እንመርምር፡፡ አንድም፤ ማታለልና ማጭበርበር የደህንነት -ማጣት፣ የሥጋት እናት ነው ይሏልና አበው፡፡ ደረጃው ይለያይ እንጂ ራስን አደጋ ላይ መጣል መሆኑን ለአፍታም አለመዘንጋት ብልህነት ነው፡፡
ለሀገራችን ፖለቲካ ብቻ ሳይሆን ለአጠቃላይ ህይወታችን፤ አንድ ተረት እጅግ ጠቃሚ ፋይዳ አለው፡፡ ይኸውም፤ “ዋናው መንገድ ቢጠፋብህ፣ መጋቢ መንገድ ፈልግ” የሚለው ነው፡፡ በሀገራችን የትግል ሂደት ውስጥ ዋናው መንገድ የጠፋበት በርካታ ጊዜ እንደነበረ የኖረና የታዘበ ሁሉ ያውቀዋል፡፡ አማራጭ መንገድ ወይም አማራጭ ዕቅድ (Plan B- እንዲሉ) የሌለው ሰው፤ ዓለም ባንድ ጊዜ የጨለመበት ይመስለዋል፡፡ “ከእንግዲህ መሄጃ መራመጃ የለም፤ ሁሉ ነገር አበቃለት” ይላል፡፡ ሌላው ቀርቶ ግን ዋናው መንገድ በዕድሳት ላይ ቢሆንስ? ብሎ እንኳ ማሰብምኮ ያባት ነው፡፡ ከሁሉ ቀዳሚው ነገር ግን ለራስ የዝግጅት ጊዜ መስጠት መሆኑን ከልብና ጥንቅቅ ባለ ሁኔታ አጢኖ መጓዝ ነው፡፡ የሚመጣውን አምስት ዓመት መንገድ  ከአሁኗ ሰዓት መጀመር ተገቢ ነው፡፡ ዋናና መጋቢ መንገዶችን በቅጡ መለየት ከአሁኑ ነው፡፡ ጊዜ የማያላላው ሰንሰለት የለም ይባላል፡፡ የለውጥ ህግ ብቻ ይቀራል እንጂ ሁሉም ነገር ይለወጣል፡፡ ስለዚህ በፅንዓት መቀጠል ይገባል፡፡ አገር በአንድ ጀንበር እንዳልተገነባች ሁሉ፣ ለውጥም በአንድ ጀንበር አይመጣም፡፡ ለውጥ አዳጊ ሂደት መሆኑን ምኔም አለመርሳት ነው፡፡ ቀና ውድድርና ፉክክር፣ የፖለቲካ ንግግርና ክርክር በማድረግ አስተሳሰብን መለወጥ የአንድ ሰሞን የቴሌቪዥን ፍጆታ አይደለም፡፡ ቻይናዎች፤
“ዕቅድህ የዓመት ከሆነ ሩዝ ዝራ፡፡
ዕቅድህ የአምስት ዓመት ከሆነ ባህርዛፍ ትከል
ዕቅድህ የዘለዓለም ከሆነ ግን ልጅህን አስተምር!”
ይላሉ፡፡ የሁልጊዜ ሥራችን ህዝብን ማስተማር መሆን አለበት፡፡ ከአሁኗ ደቂቃ ጀምሮ፡፡ በዚህ የፖለቲካ መማር ማስተማር ሂደት ውስጥ እንቅፋት አያጋጥመንም ማለት አይደለም፡፡ መስዋዕትነት የለበትም ማለት አይደለም፡፡ እንኳን የፖለቲካ መንገድ ተራውም ህይወት እንኳ በእሾክ በአረንቋ የተሞላ መሆኑን አለመዘንጋት ነው፡፡ “አገጭህን ይዞ የሚለምንህ፣ እምቢ ብትል በጥፊ ሊልህ” የሚለው ተረትም እዚህ ውስጥ እንደሚካተት አለመዘንጋት ብልህነት ነው!

የአንድነት ለዲሞክራሲና ለፍትህ ፓርቲ ፕሬዚዳንት አቶ ትዕግስቱ አወሉ፤ በቅርቡ በተካሄደው አገራዊ ምርጫ ፓርቲያቸው ያገኘውን ውጤት በፀጋ እንደሚቀበለው ጠቁመው ፓርቲው ስኬት ያላስመዘገበው በራሱ ችግር እንጂ በገዢው ፓርቲ ተጭበርብሮ እንዳልሆነ ሰሞኑን ለኢቢሲ ብቻ በሰጡት መግለጫ አስታውቀዋል፡፡ ፕሬዚዳንቱ አቶ ትዕግስቱ አወሉ ከአዲስ አድማስ ጋዜጠኛ አለማየሁ አንበሴ ጋር ባደረጉት ሞጋች ቃለምልልስ ለተለያዩ አወዛጋቢ ጥያቄዎች ምላሽ ሰጥተዋል፡፡
ምክትል ፕሬዚዳንት ስለሌለው ካቢኔያቸው፣ የፓርቲውን ውድቀት ከሚሹ አካላት ገንዘብ ተቀብለው መኪና ገዝተዋል ተብሎ ስለሚናፈሰው ወሬ፣ በዘንድሮ ምርጫ ፓርቲያቸው ባገኘው ውጤት ከመጨረሻዎቹ ተርታ ስለመሠለፉ ተጠይቀዋል፡፡ ፕሬዚዳንቱ የሰጧቸውን ምላሾች ያንብቡ፡፡
              ለአወዛጋቢ ጥያቄዎች መልስ ሰጥተዋል

     “አንድነት” ምን ውጤት ጠብቆ ነበር ወደ ምርጫው የገባው? ያገኛችሁትን ውጤትስ እንዴት አያችሁት?
አንድነት ህጋዊና ሠላማዊ ተቃዋሚ ፓርቲ ነው። ምርጫ የሠላማዊ ትግል አንዱ መገለጫ እንደመሆኑ ወደ ምርጫው ሲገባም አሸንፋለሁ ብሎ ነው፡፡ መንግስት ለመሆን የሚያበቃ በቂ ውጤት ያገኘ ፓርቲ ባይኖርና አንድነት ቢያሸንፍ ከማንኛውም ያሸነፈ ፓርቲ ጋር በጥምረት መንግስት የመመስረት አላማ ይዞ ነው ወደ ምርጫው የገባው። አንድነት ከሁሉም በላይ ግን ለዲሞክራሲያዊ ስርአት መጐልበት አስተዋጽኦ ለማድረግና በህዝብ ተወካዮች ም/ቤት ትርጉም ባለው ሁኔታ ወንበር ለማግኘት በማሰብ ነው ወደ ምርጫ የገባው፡፡
የምርጫ ውጤቱን በተመለከተ እስካሁን የተገለፀው የ442 ወንበሮች ነው፡፡ በዚህም ኢህአዴግና አጋሮቹ እንዳሸነፉ ነው የተነገረው። ስለዚህ እኛ ውጤት አላገኘንም ማለት ነው፡፡ ያገኘነው የምክር ቤት ወንበር  የለም፡፡
“አንድነት” ከሌሎቹ ተቃዋሚዎች አንፃር ያገኘው የድምጽ ብዛት ለምን ዝቅተኛ ሆነ? ቀደም ሲል ፓርቲው በተሻለ አቋም ላይ እንደነበር ይነገራል። ይሄን ጥያቄ ያነሣሁት፤ እርስዎም በተወዳደሩበት የምርጫ ክልል እጅግ ዝቅተኛ ድምጽ ማግኘትዎን ስላየሁ ነው?
ስንት ጣቢያ ላይ ነው ያየኸው?
የተወሰኑትን አይቻለሁ፡፡
እንግዲህ 57 ጣቢያ ነው ያለው፡፡ ምን ያህሉን አይተህ “ዝቅተኛ ውጤት ነው ያገኘኸው” እንዳልከኝ አላውቅም። እኔም ምን ያህል እንደሆነ ገና መረጃ እያሰባሰብኩ ነው፡፡ ግን ከአዲስ አበባ ውጪ በሌሎች እጩዎች ከኢህአዴግ ቀጥሎ ከፍተኛ ድምጽ ያገኘንባቸው ቦታዎች አሉ፡፡
ቦታዎቹን ሊጠቅሱልኝ ይችላሉ?
በደቡብ አካባቢ እንዲሁም በአማራ ክልል ከፍተኛ ውጤት አግኝተን 2ኛ የሆንባቸው ጣቢያዎች አሉ፡፡ ግን ውጤት መግለፅ አይፈቀድም፣ ምርጫ ቦርድ ማጠቃለያ ሠርቶ ውጤቱን ይፋ ያደርጋል፡፡ ለቀጣይ ምርጫ በአንድ ምርጫ ክልል የእጩዎችን ቁጥር ከ12 ያልበለጠ ለማድረግ አሁን የሚገኘው ውጤት ወሣኝነት አለው፡፡ እስከ 6ኛ ደረጃ የያዙት በቀጥታ እንዲወዳደሩ ይደረጋል፡፡ እኛም እዚያ ደረጃ ውስጥ መግባታችንን ለማወቅ የቦርዱን ጠቅላላ ውጤት መጠበቅ  ይኖርብናል፡፡
አንዳንድ ወገኖች፤ የፓርቲው የምርጫ ውጤት ዝቅ ማለት “አንድነት” በህዝብ ዘንድ ተቀባይነቱ መቀነሱን ያሳያል ይላሉ በተለይ ከቀድሞው የአንድነት ተቀባይነት አንፃር በማለት፡፡ እርስዎ ምን ይላሉ?
ከነችግሩም ቢሆን ህዝቡ ልብ ውስጥ እንዳለን በድፍረት መናገር ይቻላል፡፡ የአንድነት ችግር መነጋገሪያ የሆነው እኮ በህዝቡ ውስጥ ስላለን ነው፡፡ እኛ በህዝቡ ውስጥ ነን ብለን እናምናለን። የእርስ በእርስ ውዝግቡ ለትግሉ ስኬት በጐ ያልሆነ አስተዋጽኦ አለው፡፡ ይሄን ሁሉ ታግሎ ማለፍ ይጠይቃል፡፡ እኛ በተለያዩ አደረጃጀቶቻችን አማካኝነት በህዝቡ ውስጥ እንዳለን እናውቃለን፡፡ ለዚህ ማሣያው የምርጫ ውጤት ብቻ አይደለም። ሀገራችን ለዲሞክራሲ ገና ጀማሪ እንደመሆኗ ነገሮችን ከነችግሩ መቀበል ያስፈልጋል፡፡
“አንድነት” ከአመራር ውዝግቡ በፊት ከሁሉም ተቃዋሚዎች የበለጠ በርካታ እጩዎችን እንደሚያቀርብ አስታውቆ ነበር፡፡ እናንተ 92 እጩዎች ብቻ ነው ያቀረባችሁት፡፡ ይሄ ከአመራር ለውጡ በኋላ ፓርቲው መዳከሙን ወይም ብዙዎች ከፓርቲው መሻሻቸውን አያሳይም?
አሁን ተዳክሟል፣ አልተዳከመም ለማለት ያስቸግራል። እኔ አመራሩን ስለያዝኩት ተዳክሟል ሊባል አይችልም፡፡ የበፊቱ አመራር ውስጥም ነበርኩበት፤ ዝም ብዬ መጥቼ የተቀመጥኩ ሰው አይደለሁም፡፡ ፓርቲው መጀመሪያም ድክመት አለው፡፡ ምናልባት በወቅቱ እዚያም እዚህም  የነበሩ ጩኸቶችን ሳታዳምጡ አልቀራችሁም። ያ ጥንካሬን አያሣይም፡፡ ፓርቲው ድክመት ነበረበት። አሁንም ፓርቲው ወደቀ አይባልም፤ በመካከለኛ ደረጃ እየተጓዘ ነው፡፡ በአመራር ደረጃ የተፈጠረው ችግር አሉታዊ ነገሮች አሉት፡፡ ውዝግቡ የወሰደው ጊዜ በቂ እጩዎች ማቅረብ እንዳንችል አድርጐናል። ፓርቲው ለሁለት አመት ያቀደውን ማከናወን አልቻለም፡፡ እቅዱ የጨነገፈበት ምክንያት የአመራሩ ውዝግብ ነው፡፡ እጩዎችን ለማቅረብ 7 ቀን ብቻ ነው የተሠጠን፡፡ ስለዚህ የተፈጠረው ችግር እቅዳችንን አፋልሶታል፡፡ እጩዎችንም በበቂ ሁኔታ እንዳናቀርብ አድርጐናል፡፡ በችግር ውስጥ እያለን በአጭር ጊዜ 92 እጩዎችን ማስመዝገብ በራሱ ትልቅ ስኬት ነው፡፡
ያለ ፓርቲው ሙሉ አባላት ተቀባይነት የእርስዎ ወደ አመራር መምጣት “አንድነት”ን እንዳልነበር አድርጐታል፣ የፓርቲውን መዋቅርም አፈራርሶታል የሚሉ ወገኖች አሉ፡፡ እርስዎ ለፓርቲው መዳከም ተጠያቂ አይደለሁም ነው የሚሉት?
ተጠያቂ አይደለሁም፤ ምክንያቱም በህግ አግባብ የተሸነፉት ሰዎች አይደሉም እንዴ “አንድነት ፈርሷል የለም” ብለው አባላትን ወደ “ሠማያዊ” ያስኮበለሉት። “የሠማያዊ” አብዛኞቹ እጩዎች የማን ናቸው? የ “አንድነት” ናቸው፡፡
ግን እኮ አባላቱ ወደ “ሠማያዊ” የኮበለሉት የእርሶን አመራር ባለመቀበል እንደሆነ ነው የሚነገረው…?
ይሄንማ የኔ ተቀባይነት ማጣት ማሳያ ሆኖ ሊቀርብ አይገባም፡፡ የቀሩትንም አባላት ማሰብ አለብን፡፡
የቀሩ አባላት ቢኖሩም ፓርቲውን ከምስረታ ጀምሮ በአመራርነት ለረጅም ጊዜ ያገለገሉና ያደራጁ ሰዎች በአብዛኛው የእርስዎን አመራር አልተቀበሉትም ይባላል…
ተው እንደሱ አይደለም… ዋናዎቹ አልሄዱም። እስቲ ቁጠርልኝ… የትኛው አመራር የኔን አመራር አልቀበልም ብሎ ሄደ? አመራር ሳይሆን “እኛ ብቻ” የሚሉት ናቸው የሄዱት፡፡ ከዚያ ውጪ የቢሮ ሠራተኞች ሄደው ሊሆን ይችላል፡፡ በተረፈ ሚዲያውም ሆነ ሌላው የራሱን ስሜት ብቻ ነው የሚያራግበው፡፡
አሁን በእርስዎ አመራር ስር ምን ያህል አባላት አሉ?
በቁጥር ይሄን ያህል አልልህም፤ አንተም የሄዱትን በቁጥር ልትጠቅስልኝ አትችልም፡፡ ስለዚህ ያሉን አባላት ይሄን ያህል ናቸው ልልህ አልችልም። ፓርቲው እኮ አሁንም አደረጃጀቱንና መዋቅሩን አጠናክሮ እየሠራ ነው።
በክልሎች ያለው መዋቅራችሁ በአብዛኛው እንደፈራረሰ ይነገራል…
መዋቅር ቢኖረን አይደለም እንዴ 92 እጩዎችን በ7 ቀናት ማስመዝገብ የቻልነው፡፡ መዋቅራችንም ሆነ አደረጃጀታችን እንዳለ ነው ያለው፡፡ ያ ሁሉ “አንድነት”ን አፍርሱና ውጡ ጉትጐታ ሣይበግራቸው አባላቱ አብረውን አሉ፡፡ በየፕሬሱ ፓርቲውን እንዲለቁ ሲጐተጐት ነበር። ለነገሩ ፕሬሱ ምን አይነት አዝማሚያ እንደነበረው እኛ እናውቃለን፡፡ አንዳንድ ጊዜ ነፃ ሃሳብ ሣይሆን ግለሰብን በመውደድ የህዝብ ግንኙነት ስራ የሚሠሩ ፕሬሶች አሉ፡፡ ግን ያሁሉ ከሽፎ ምርጫው ተካሂዷል፡፡ የምርጫ ውጤት ማጣት የኛ ችግር ብቻ አይደለም፤ ሌሎችም ፓርቲዎች በዜሮ ድምር ተባዝተዋል፡፡
የአመራር ውዝግቡ ባይፈጠር ግን “አንድነት” ከየትኛውም ፓርቲ በተሻለ ዝግጅት ወደ ምርጫው ገብቶ ውጤት ማስመዝገብ ይችል ነበር ብለው የሚቆጩ ወገኖች አሉ፡፡ እርስዎ ምን ይላሉ?
የተሳሳተ ግንዛቤ ነው፡፡ “አንድነት” ሠዎች እንደሚሉት አይደለም፡፡ የግለሰቦች ችግር የነበረበት ፓርቲ ነው። ፕሮግራሙን ከማስፈፀም አንፃር ሌላ ችግር የነበረበት ፓርቲ ነው፡፡ ምንም ውዝግብ ባይፈጠር እንደውም በራሱ ችግሮቹ ምክንያት ወደ ምርጫው ሁሉ ላይገባ ይችል ነበር፡፡ የአስተሳሰብ ችግር በውስጡ የነበረበት ፓርቲ ነው፡፡ እነዚያ ሰዎች እኮ ፓርቲውን አድምተውታል፤ አቁስለውታል፡፡ አሁን እያገገመ ነው ያለው፡፡
አንድነት እኮ አሁን ብቻ አይደለም አመራሩ የተቀየረው፡፡ ከዶ/ር ነጋሶ በኋላ እንኳ እኔ ሦስተኛ ሰው ነኝ፡፡ እነዚህ ጠንካራ ነበሩ የሚባሉት ግለሰቦች የ3 ወር የአመራር እድሜ ነው የነበራቸው፡፡ እንዴት ነው በ3 ወር ጊዜ ውስጥ ተገምተው ጠንካራ ናቸው የሚባሉት? እንደገና የመጡትም በአሻጥር ነው፡፡ በአመራር ላይ ሲሰሩ የነበረው አሻጥር ነው እነሱኑ መልሶ የበላቸው። “አንድነት” ተዳክሟል የሚባል ከሆነ፣ በኔ አመራር ሳይሆን ተያይዞ በመጣ ችግር ነው የደከመው፡፡ ችግሩ የጀመረው በዶ/ር ነጋሶ አመራር ጊዜ ነው፡፡ “እሣቸው ጠንካራ ስለነበሩ  አቻችለው ይዘው ቆዩ፤ ዛሬ ትዕግስቱ ስለያዘው ወደቀ” ማለት አይቻልም፡፡
እርስዎ ከዚህ በፊት ለፓርቲው ፕሬዚዳንትነት ተወዳድረው 1 ድምጽ ብቻ ነው ያገኙት ይባላል፡፡ እውነት ነው?
ይሄ ብዙ ጊዜ ይባላል፡፡ በዲሞክራሲ የማያምኑ ሰዎች የሚያወሩት ነው፡፡
እርስዎ 1 ድምጽ ብቻ ማግኘትዎ ግን እውነት ነው?
እሱን የሚያውቀው በወቅቱ የነበረው አስመራጭ ኮሚቴ ነው፡፡ ለፕሮፓጋንዳ ተብሎ የሚወራ ነገር ነው። ይሄን ጥያቄ ደግሞ በዚህ ሰአት እንድጠየቅ ፈጽሞ አልፈልግም፡፡ ቆይ ለምን አሁን ስለተመረጥኩበት 160 ድምጽ አታነሳም፡፡ እሱን ለምን አትናገሩትም፡፡ ደግሞ አሁን ያለፈ ታሪክ አይደለም ማውራት ያለበን፡፡
ወደሱም ልመጣ ነበር እኮ… በውድድሩ አንድ ድምጽ ብቻ አግኝተው ብዙም ሣይቆዩ እንዴት በ160 ድምጽ ተመረጡ… የሚለውን የሚጠይቁ ወገኖች አሉ…
ይሄ ፍፁም ዲሞክራሲያዊ ያልሆነ፣ የፀለምተኝነት አስተሳሰብ ነው፡፡ እንዲህ አይነት ነገር የለም፡፡ ትናንት 1 ድምጽ አግኝቶ፣ ዛሬ እንዴት 160 ድምፅ ሊያገኝ ይችላል? የሚለው አያስኬድም። ይሄ የሂሣብ ጉዳይ አይደለም፡፡ ነገሩ ለፕሮፓጋንዳ ዓላማ የሚውል ስለሆነ አሁን ምንም የምለው ነገር የለኝም።
ቀደም ሲል ፓርቲው ከአሜሪካና በተለያዩ ሃገራት ካሉ ደጋፊዎቹ ሰፊ የገንዘብ ድጋፍ እንደሚያገኝ ሲገለፅ ነበር፡፡ አሁንስ ድጋፉ ሳይቋረጥ ቀጥሏል? ወይስ…
ፓርቲው በፊት ስንት ያገኝ እንደነበር ስለማናውቅ ይሄን ለመግለጽ ይከብደናል፡፡ እኛ የምናገኘውን የድጋፍ መጠን በተመለከተም ለመናገር የምንገደድ አይመስለኝም፡፡ ፓርቲው ተቋም እንደመሆኑ ድጋፍ አለው፡፡ በአመራር ደረጃ የግለሰቦችን መፈራረቅ ተመልክተው የሚሸሹ ሰዎች የሉም፡፡ “እኔ ፓርቲውን ካልመራሁት ደክሟል” ማለት፣ የጨለምተኝነት አስተሳሰብ ነው እንጂ ዲሞክራሲያዊ አስተሳሰብ አይደለም፡፡ “አንድነት” ደግሞ እነዚህን ሰዎች ሠርጐ ገቦች አድርጐ ነው የሚወስዳቸው፡፡ ባህሪው አይደለማ!
ከምርጫ ቦርድ ለምርጫው ማስፈፀሚያ የተሰጣችሁን ግማሽ ሚሊዮን ብር ገደማ ለምን ተግባር ነው ያዋላችሁት?
ሙሉ ለሙሉ ለምርጫው ቅስቀሳ ነው  ያዋልነው፡፡
አንዳንድ የፓርቲው እጩዎች ግን በገንዘብ እጦት የቅስቀሳ ፖስተራቸውን እንኳ
ሳይለጥፉ እንደቀሩ ይነገራል…
የተሳሳተ መረጃ ነው፡፡ ለእጩዎች ገንዘብ ሰጥተናል። በስንፍና ያልለጠፈ ሊኖር ይችላል፡፡ እኛ ግን ገንዘቡን ለፓርቲው ሙሉ እንቅስቃሴ ነው ያዋልነው፡፡ ሌላው የጀነራል ኦዲተር ስራ ነው፡፡
አሁንም በመካከላችሁ የአመራርና የአባላት ቅራኔና መከፋፈል እንዳለ ይወራል…?
የለብንም፡፡ ችግር ያለበት አመራር ካለ ሊጠየቅ ይችላል፤ እኔ እስከማውቀው ድረስ የአመራር መከፋፈል  የለም፡፡
ፓርቲው ምክትል ፕሬዚዳንት የለውም፡፡ ለምንድን ነው?
አልሾምንም!!
እስካሁን ያልተሾመበት የተለየ ምክንያት አለው?
ምንም ምክንያት የለውም፡፡ በቃ ለቦታው የሚሆን ብቃት ያለውን ሰው ፈልገን እስከምናገኝ ድረስ ነው፡፡ እኛ እኮ ገና አሁን ነው ከችግር ውስጥ የወጣነው፡፡
የእርስዎን ካቢኔ ሊነግሩኝ ይችላሉ፡፡ እነማንን ያካትታል?
አሁን ካቢኔውን ማሳወቅ የሚጠበቅብኝ አይመስለኝም፡፡
ግን ፓርቲው ካቢኔ አለው?
አዎ አለው! ግን አሁን ማሳወቅ አይጠበቅብኝም፡፡
ፓርቲው ግልጽ አሠራር የሚከተል ከሆነ፣ ደጋፊዎቹና ህዝቡ ካቢኔውን ቢያውቁ ምን አለበት?
ተወው እሱን! ከአመራርነት ወጣን የሚሉ ሰዎች “የካቢኔ አባል ነን” የሚሉ ከሆነ፣ እነሱን አግኝተህ ጠይቅ። በ“አንድነት” ውስጥ መከፋፈል ተፈጥሯል የምትለኝም አያስደንቀኝም፤ ብዙ ፍላጐት ያለበት ቤት ስለሆነ ሰዎች የየራሳቸውን ነገር ሊፈጥሩ ይችላሉ፤ ነገር ግን የምንመራው በስርአት ስለሆነ ስርአቱ ራሱ ይገዛናል፡፡
ቀደም ሲል “አንድነት” አልፈርምም ያለውን የስነ ምግባር ደንብ ፈርማችሁ,ኧ የፓርቲዎች የጋራ ምክር ቤት የመግባት እቅድ አላችሁ?
አሁን እቅድ አለን የሚል መልስ የለኝም፡፡ ምክንያቱም ቀደም ሲል ከ “መድረክ” ጋር ስለነበርን የመድረክን አቋም ነው ፓርቲው ያራመደው፤ አሁን ከመድረክ ጋር አይደለንም፡፡ በሌላ በኩል ከመድረክ ጋር ያለን ግንኙነትም አለ፡፡ እስካሁን ግን በምርጫ ሂደት ውስጥ ስለነበርን በጉዳዩ ላይ ተወያይተን ውሳኔ አልሰጠንበትም። በቀጣይ የሚታይ ይሆናል። የፓርቲዎች የጋራ ምክር ቤት አባል መሆን ያለመሆን ጉዳይም ሆነ መድረክ መልሶ በመቀላቀል ላይ የተወሰነ ነገር የለም፡፡
“አንድነት በአመራር ሽኩቻ ምክንያት ተቀባይነት እያጣ መጥቷል” የሚለው ጉዳይ ከፓርቲው የወደፊት እጣ ፈንታ አንፃር አያሳስቦትም?
አያሳስበኝም፡፡ ምክንያቱም “አመራር ነን” ብለው “አመራር አይደላችሁም” የተባሉት ሰዎች፣ ትክክል ናቸው የሚል አዝማሚያ ስላለ ነው፡፡ ፓርቲዎች ለህግ ተገዢ መሆን አለባቸው፡፡ እኛ በህግ አሸነፍን፤ እነሱ ግን በኔትወርክ ለመጓዝ ነበር ሃሳባቸው፡፡
አንዳንድ ወገኖች ከመንግስት ከፍተኛ ድጋፍ እንዳለዎት ይናገራሉ፡፡ በዚህ ላይ ምን ይላሉ?
ምንም ድጋፍ የለኝም! ህግን ከማስከበር አኳያ መንግስት ድጋፍ በማድረጉ ሃላፊነቱን ነው የተወጣው። እንዴ! እነሱ በኔትወርክ የሄዱት እኮ ለባለስልጣኖች ድጋፍ ነበር፤ ግን አልተሳካም። እዚህ ቤት ከዚህ በኋላም ባለፈው የተፈጠረው ስሜት ሊፈጠር ይችላል፤ ማንም ዋስትና የለውም። አሁንም የቡድን ስሜቶች ያሉበት ቤት ነው፡፡ አሁን “አንድነት”ን የሚመራው አንድ አመራር ነው። እነዚህ ሰዎች በፓርቲው ስም እንንቀሳቀሳለን ቢሉ በህግ ይጠየቃሉ፡፡ ይሄን የሚያራግብ የሚዲያ አካልም ከተጠያቂነት አያመልጥም፡፡
የአንድነትን አመራር ለመከፋፈል ላደረጉት ውለታ የፓርቲውን መዳከም ከሚፈልጉ ወገኖች  ገንዘብ ተሰጥቶታል፣ መኪናም ገዝተዋል…” የሚሉ መረጃዎች ይናፈሳሉ
ማን ነው ያለው?
“ከአንድነት” የወጡ የቀድሞ አባላት በማህበራዊ ሚዲያው በስፋት እየፃፉበት ነው
ማህበራዊ ሚዲያው ሃላፊነት የሚሠማው ስላልሆነ አላምንበትም፡፡ በሶሻል ሚዲያ ለሚወራው ነገር ብዙም ትኩረት ስለማልሰጠው በዚህ ላይ ጊዜዬን ማጥፋት አልፈልግም፡፡ በማላምንባቸው ሚዲያዎች የቀረበ ስም ማጥፋት ስለሆነ አልቀበለውም፡፡
ግን እኮ ይሄን የሚሉት የፓርቲው የቀድሞ አመራሮች ናቸው፡፡ እናንተም በሬዲዮ የፓርቲውን ገንዘብ ለግል ጥቅማቸው አውለዋል ብላችሁ ስትወነጅሉ ነበር፡፡ የእርስዎን በተመለከተ ለምን ቀጥተኛ ምላሽ አይሰጡኝም?  
እኔ የገዛሁት መኪናም የለም፡፡ ያገኘሁት የውለታ ገንዘብም (Reward) የለም፡፡ “ሪዋርድ” ላገኝ የምችልበት መንገድም የለም፤ በዚያ ላይ ፓርቲውን አላፈረስኩም፤ ይዤ ነው የቀጠልኩት።
ለ20 አመት ያህል በተቃዋሚ ውስጥ ያለሁ ሰው ነኝ። ከኢህአዴግ ጉርሻ አግኝቷል የሚሉት  በሃሳብ የበላይነት ተሸንፈው የወጡት ናቸው፡፡
“ሠማያዊ” ፓርቲን የመሠረቱት ሰዎችም ዛሬ ጀግና ሊባሉ በፊት እንዲህ ተብለው ነበር፡፡ እዚህ ፓርቲ ውስጥ ሲታገሉ ለእስር የተዳረጉት እነ ሃብታሙ አያሌውም ታስረው እንኳ አያምኗቸውም ነበር…ከነዚህ ሰዎች ጋር ነው እንዴ የኖርነው፡፡
እናንተ የታሠሩትን የአንድነት አባሎችና አመራሮች ትጠይቃላችሁ?
አዎ፤ እኔ አልቻልኩም እንጂ የኛ ልጆች ሄደው ይጠይቃሉ፡፡
የታሠሩት የፓርቲው አመራሮች ለእርሶ ድጋፍ እንዳላቸው አረጋግጠዋል?
እነሱ በህግ ጥላ ስር ስለሆኑ በዚህ ፓርቲ ውስጥ ያላቸውን ተሳትፎ ለማወቅ ያስቸግራል። የነሱን ፍላጐት ለመረዳት ግን አልሞከርንም፡፡ እኔ እንደምረዳው… “አንድነት” የታገሉለት ፓርቲ እንደመሆኑ… ከሱ ውጪ ሌላ አተያይ አላቸው የሚል እምነት የለኝም፡፡ እኛ የምናስበው፤ የኛ አርአያና የትግል ጽናት ተምሣሌዎች መሆናቸውን ነው፡፡ ትግላችንም እንዲፈቱ ነው፡፡

አራት ታላላቅ የአፍሪካ ኩባንያዎች ለመጨረሻው ዙር ደርሰዋል

    የዓለም የኢኮኖሚ ፎረም በአፍሪካ ፈጣን እድገት እያስመዘገቡ የሚገኙ ስኬታማ ኩባንያዎች  በማለት ለመጨረሻው ዙር ከመረጣቸውና ለቀጣዩ ሽልማት ካጫቸው አራት ግዙፍ የአህጉሪቱ አየር መንገዶች አንዱ የኢትዮጵያ አየር መንገድ መሆኑን አስታወቀ፡፡
ፎረሙ ከአፍሪካ አልፈው በአለማቀፍ ደረጃ የኢኮኖሚው ዘርፍ መሪ የመሆን አቅም ያላቸው የአህጉሪቱ ኩባንያዎችን ለመምረጥ ባከናወነው ሂደት፣ ለመጨረሻው ዙር የደረሱትን 4 የተለያዩ የአፍሪካ አገራት ኩባንያዎች ዝርዝር ሰሞኑን በደቡብ አፍሪካ ኬፕታውን ባካሄደው ጉባኤው ይፋ አድርጓል፡፡ ለመጨረሻው ዙር በዕጩነት የቀረቡት አራቱ ኩባንያዎች የኢትዮጵያ አየር መንገድ፣ የዝምባዌው የንግድና የሆቴል ኢንቨስትመንት ኩባንያ ሜክሌስ፣ የደቡብ አፍሪካው ሲሚንቶ አምራች ፒፒሲ እና የናይጀሪያው ነዳጅ አምራች ኩባንያ ዋልተርስሚዝ ፔትሮማን ኦይል ናቸው፡፡
በዓለም የኢኮኖሚ ፎረም የኒው ሻምፒየንስ ማኔጂን ዳይሬክተርና ሃላፊ የሆኑት ዴቪድ አኪማን በጉባኤው ላይ ባሰሙት ንግግር፣ ፎረሙ ሃላፊነት የሚሰማው የኢኮኖሚ እድገት በማስመዝገብ፣ የስራ ዕድል በመፍጠርና የስራ ፈጠራን በማስፋፋት ረገድ በአፍሪካ በግንባር ቀደምትነት ለሚመሩት ለእነዚህ አራት ኩባንያዎች እውቅና በመስጠቱ ኩራት ይሰማዋል ብለዋል፡፡
ኩባንያዎቹ በትርፋማነት እድገት፣ በፈጠራ የታገዙ የንግድ እንቅስቃሴዎችን ተግባራዊ በማድረግና አመራር በኩባንያዎች እንቅስቃሴ ላይ ያለውን ሚና በተግባር በመግለጽ ረገድ በአህጉሪቱ የላቁ ሆነው በመገኘታቸው ለመጨረሻው ዙር መብቃታቸው ተገልጧል፡፡
በመጪው መስከረም ወር በቻይና በሚካሄደው የዓለም የኢኮኖሚ ፎረም የኒው ሻምፒዮንስ አመታዊ ጉባኤ ላይ በሚከናወን ስነስርዓት ከአራቱ ኩባንያዎች አሸናፊው ይፋ እንደሚደረግ ይጠበቃል።

አስከሬኑ ወደ ለንደን ተወስዶ እንዲመረመር ተጠየቀ

       በደቡብ ሱዳን ዐማፅያን ዘንድ ከፍተኛ ተሰሚነት የነበራቸው ዋኒ ቶምቤ ላኮ በአዲስ አበባ በመኖርያ አፓርትመንታቸው ውስጥ ሞተው ተገኙ፤ ቤተሰቦቻቸው አስከሬናቸው ወደ ለንደን ተወስዶ እንዲመረመር ጠይቀዋል፡፡
በለንደን በስደት ይኖሩ የነበሩት ቶምቤ፤ ባለፈው ዓመት ወደ ኢትዮጵያ በመምጣት በቀድሞው የደቡብ ሱዳን ምክትል ፕሬዝዳንት ሬክ ማቻር የሚመራውን የመንግሥት ተቃዋሚ ቡድን ተቀላቅለዋል፡፡ በተቃዋሚው ቡድን ውስጥ የተለየ የኃላፊነተ ቦታ ባይሰጣቸውም ሚያዚያ አጋማሽ ላይ በተደረገው የዐማፅያኑ የከፍተኛ ኃላፊዎች ስብሰባ ላይ ተሳታፊ ነበሩ፡፡ የተቃዋሚው መሪ ሬክ ማቻር የቶምቤን ሞት ተከትሎ በሰጡት መግለጫ፣ የእርሳቸው መሞት ለደቡብ ሱዳን፣ ለተቃዋሚ ቡድን እና ለቤተሰቦቻቸው ከፍተኛ ጉዳት እንደሆነ በመግለጽ ለቤተሰቦቻቸው መጽናናትን ተመኝተዋል፡፡
የሞታቸውን መንስኤ በተመለከተ ከሐኪም የተሰጠ መረጃ ባይኖርም በቅርብ የሚያውቋቸው ጓደኞቻቸው በልብ ድካም ህይወታቸው አልፎ ሊሆን እንደሚችል ተናግረዋል፡፡ የቶምቤ ቤተሰቦች በበኩላቸው፣ አስከሬናቸው ለንደን ሄዶ እንዲመረመር መጠየቃቸውን “ሱዳን ትሪቢዩን” ዘግቧል፡፡
ቶምቤ፣ በደቡብ ሱዳን የተቀሰቀሰውን የእርስ በርስ ጦርነት ተከትሎ በአሜሪካ፣ በካናዳ እና በአውስትራልያ በመዘዋወር ደቡብ ሱዳናውያን አሁን በሥልጣን ላይ ያለውን መንግሥት ለመጣል የትጥቅ ትግሉን እንዲቀላቀሉ ሰፊ ቅስቀሳ ማድረጋቸው ይነገርላቸዋል፡፡

  ፖሊስ የ10 ቀን የምርመራ ጊዜ ጠይቆባቸዋል

    በደቡብ ክልል የስልጤ ዞን ምሥራቅ አዘርነት በርበሬ ወረዳ፣ የቂልጦ ጎሞሮ ቅድስት ማርያም ቤተ ክርስቲያን ሰበካ መንፈሳዊ ጉባኤና የደብሩ ሕንፃ አሠሪ ኮሚቴ አባላት “ሃይማኖትን ከሃይማኖት ለማጋጨት ተንቀሳቅሳችኋል” በሚል በፖሊስ ቁጥጥር ሥር ውለው ፍርድ ቤት ቀረቡ፡፡
የወረዳው ፖሊስ፣ ባለፈው ሳምንት ዓርብ እና በዚኽ ሳምንት ሰኞ ስድስት የሰበካ ጉባኤውንና የቤተ ክርስቲያኒቱን የሕንፃ አሠሪ ኮሚቴ አባላት በቁጥጥር ሥር በማዋል በቂልጦ ወረዳ ፍርድ ቤት አቅርቧቸዋል፡፡
ግለሰቦቹ “የድረሱልኝ ጥሪ” በሚል “ሃይማኖትን ከሃይማኖት የሚያጋጭ ጽሑፍ ጽፈው በፌስቡክ አሰራጭተዋል” ሲል ፖሊስ ለፍርድ ቤቱ አስረድቷል፡፡ ግለሰቦቹ “የድረሱልኝ ጥሪ”  በሚል ደብዳቤ መጻፋቸውን ቢያምኑም በፌስቡክ አለመልቀቃቸውን ለፍርድ ቤቱ ገልጸዋል፡፡ ፖሊስ በቁጥጥር ሥር በዋሉት ግለሰቦች ላይ የማጣራው ነገር አለ በሚል የ21 ቀን የምርመራ ጊዜ የጠየቀባቸው ቢሆንም ፍርድ ቤቱ የ10 ቀን የጊዜ ቀጠሮ ፈቅዶለታል፡፡
የወረዳው የጸጥታ ዘርፍ ሓላፊ አቶ ቶፊቅ ከድር፣ ስለ ጉዳዩ በስልክ ጠይቀናቸው፤ “በሕግ የተያዘ ጉዳይ በመሆኑ አስተያየት ለመስጠት አልችልም” ብለዋል፡፡
በፖሊስ ቁጥጥር ሥር የሚገኙት የቂልጦ ቅድስት ማርያም ሰበካ ጉባኤ እና ሕንፃ አሠሪ ኮሚቴ አባላት÷ ሊቀ መንበሩ መ/ር የማርያም ወርቅ ተሻገር፣ መ/ር ሀብታሙ ተካ፣ አቶ ሙሉጌታ አራጋው፣ ወ/ሪት ንጋት ለማ፣ አቶ ማስረሻ ሰይፈ እና አቶ ማሩ ለማ ሲሆኑ በወረዳው የከፍተኛ ሁለተኛ ደረጃ መሰናዶ ት/ቤት፣ የፖሊስ፣ የጤና እና የግብርና ጽ/ቤቶች እንዲሁም የባንክ ቅርንጫፍ ሠራተኞች ናቸው፡፡
‹‹የድረሱልኝ ጥሪ›› በሚል ርእስ የተሰራጨውና የደብሩን የሰበካ ጉባኤ ጽ/ቤት ማኅተም የያዘው ጽሑፍ÷ በስልጤ ዞን በምሥራቅ አዘርነት በርበሬ ወረዳ የሚኖሩ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ሃይማኖት ምእመናን፣ በሃይማኖታዊ ማንነታቸው ላይ ባለሥልጣናት ይፈጽሙብናል ባሏቸው ግፎች መማረራቸውን፣ የአምልኮ ነጻነታቸው እና ሠርተው የመኖር ዋስትናቸውም አደጋ ላይ መውደቁን ያስረዳል፡፡
ኢትዮጵያ የሃይማኖት እኩልነት የተረጋገጠባት መሆኗን በፅሁፋቸው የጠቆሙት ምእመናኑ፣ ስለሚፈጸምባቸው ግፍና ሥቃይ ለወረዳው የፖሊስ እና የሕግ አካላት በየደረጃው ቢያመለክቱም የአስተዳደሩ መዋቅር እና አሠራር ያልተገባ “ሕጋዊ ሽፋን” በመስጠቱ የጥቃቱ ስልት ዐይነት እየጠነከረ መጣ እንጂ መፍትሔ አለማግኘታቸውን ተናግረዋል፡፡
በየመኖሪያ አካባቢያችንና በሥራ ቦታዎች እየደረሰብን ነው ያሉት እስር፣ እንግልት፣ ዛቻ፣ እንዲሁም በመ/ቤት ከደረጃ ዝቅ መደረግና መታገድ እና መባረር እየተጠናከረ መምጣቱን የገለጹት ምእምኑ፣ ድርጊቱ የተባባሰው፤ የቤተ ክርስቲያን መሥሪያ ቦታ ተረክበው የሀገረ ስብከቱ ሊቀ ጳጳስ የመሠረት ድንጋይ ካስቀመጡበት ከጥቅምት 24 ቀን 2007 ወዲህ መሆኑን አመልክተዋል፡፡
ለመንግሥት እና ለቤተ ክህነት አካላት አቤቱታቸውን ያሰሙበት “የድረሱልኝ ጥሪ” የሚለው ይኸው ጽሑፍ፣ የሀገረ ስብከቱን ፈቃድ በመጠየቅ የተዘጋጀ መሆኑን የገለፁት ምእመናኑ በአንዳንድ ባለሥልጣናት የሚደርስባቸውን ሥቃይ በመዘርዘር መፍትሔ የጠየቁበት እንደሆነ ጠቁመው፤ “ታምኑበታላችኹ ወይስ አታምኑበትም” እየተባለ ሃይማኖታዊ ግጭት እንደቀሰቀስንና የወረዳውን ስም እንዳጠፋን ተደርገን መታየታችን አሳዝኖናል ሲሉ ርምጃውን ተቃውመዋል፡፡
ቀድሞ ያስቀድሱበትና የመካነ መቃብር አገልግሎት ያገኙበት የነበረው የቅዱስ ጊዮርጊስ ቤተ ክርስቲያን ከ20 ዓመት በፊት መቃጠሉን ያስታወሱት ምእመናኑ፣ በምትኩ የሚያሠሩት የሕንፃ ቤተ ክርስቲያኒቱ መቃኞ በመጪው ሰኔ 21 ቀን የሚመረቅ መሆኑንም ገልጸዋል፡፡
የሃዲያ እና ስልጤ ሀገረ ስብከት ሥራ አስኪያጅን ጨምሮ የወረዳ ቤተ ክህነቱ ሓላፊዎች እንዲሁም የሰበካው ቤተ ክርስቲያን ምእመናን ከወረዳው አስተዳደር ጋር በጉዳዩ ላይ እየተነጋገሩበት እንደሆነ ምንጮች ጠቁመዋል፡፡ በሌላ በኩል ‹‹የድረሱልኝ ጥሪ›› በሚል በፌስቡክ ተሰራጭቷል ለተባለው ጽሑፍ የታሰሩት የሰበካ ጉባኤ አባላት ማስተባበያ እንዲሰጡና መሳሳታቸውን አምነው ይቅርታ እንዲጠይቁ በማግባባት ከእስር ለማስፈታት ጥረት እየተደረገ መኾኑንም ምንጮቹ አክለው ገልፀዋል፡፡

Saturday, 30 May 2015 12:52

የትንፋሽ ህክምና

ክብደትን ለመቀነስ

በመሬት ላይ እግርዎን አጣጥፈው ይቀመጡ፤

ወገብዎን ቀና፣ ሆድዎን ወደ ውስጥ ሳብ ያድርጉት፤

ግራ እጅዎን ጉልበትዎ ላይ ያድርጉ፣ በቀኝ እጅዎ

ሌባ ጣት የግራ አፍንጫዎን ይዝጉት፡፡ ወደ ውጪ

ይተንፍሱ፣ ይ ህንን በ መደጋገም ይ ከውኑ። በቀን

ውስጥ በተመችዎ ጊዜ የቻሉትን ያህል ለመሥራት

ይሞክሩ፡፡ በሶስት ወራት ጊዜ ውስጥ ክብደትዎ

መቀነሱንና የምግብ ፍላጎትዎ መቆጠቡን

ይታዘባሉ። እስቲ አሁኑኑ ይሞክሩት …

(ምንጭ፡- ታይም መፅሔት

June 2011)