Administrator

Administrator

Monday, 06 October 2014 08:33

የፍቅር ጥግ

አንድ ወጣትና አንዲት ኮረዳ በሞተር ሳይክል ይጋልባሉ፡፡ ሞተሩ 100 ሜትር በሰዓት ይከንፋል፡፡
ኮረዳዋ፡- ቀስ በል በናትህ፤ በጣም ያስፈራል!
ወጣቱ፡- አይዞሽ፤ ደስ ይላል እኮ!
ኮረዳዋ፡- ምንም ደስ አይልም፤ በናትህ በጣም ነው የሚያስፈራው!
ወጣቱ፡- እንግዲያውስ እወድሃለሁ በይኝ፡፡
ኮረዳዋ፡- እሺ እወድሃለሁ፤ ግን ቀስ በል!
ወጣቱ፡- በይ ሄልሜቴን ውሰጂና ጭንቅላትሽ ላይ አጥልቂው፤ እኔን አስጨንቆኛል፡፡
በነጋታው በወጣ ጋዜጣ ላይ፡- አንድ ሞተር ሳይክል ፍሬን በጥሶ ከአንድ ህንፃ ጋር በመጋጨቱ ሞተሩ ላይ ከነበሩት ሁለት ሰዎች አንደኛው ህይወቱ ወዲያው አልፏል፡፡ የሆነው እንዲህ ነው፡- ጥንዶቹ ግማሽ መንገድ እንደከነፉ፣ ፍሬኑ እምቢ ማለቱን ወጣቱ ተገንዝቧል፡፡ ነገር ግን ፍቅረኛው ይሄን እንድታውቅ አልፈለገም፡፡
ይልቁንም ለመጨረሻ ጊዜ እወድሃለሁ የሚለውን ጣፋጭ ዜማዋን ማዳመጥ ስለፈለገ እንድትልለት ጠየቃት፡፡ ከዚያም ሄልሜቱን (ከአደጋ መከላከያውን) ከራሱ ላይ ወስዳ እንድታጠልቀው አደረጋት፡፡
ወጣቱ ሄልሜቱን ባለማድረጉ ለሞት እንደሚዳረግ ያውቅ ነበር፡፡ እሱን ያሳሰበው ግን የፍቅረኛው ህይወት ነው፡፡ ስለዚህም እሱ ሞቶ፤ እሷን አተረፋት፡፡  

Monday, 06 October 2014 08:32

የፀሐፍት ጥግ

ስለፖለቲካ

ፖለቲካ በጣም ብርቱ ጉዳይ ስለሆነ ለፖለቲከኞች የሚተው አይደለም ወደሚል ድምዳሜ ደርሻለሁ፡፡
ቻርልስ ደጎል
በእኛ ዘመን ከፖለቲካ መራቅ የሚባል ነገር የለም፡፡ ሁሉም ጉዳዮች ፖለቲካዊ ጉዳዮች ናቸው፡፡
ጆርጅ አርዌል
ፖለቲካ ፍልስፍናን በተካበት ዓለም ውስጥ ነው የምንኖረው፡፡
ጆሲ ማርያዲ ኢካዲ ኪውይሮዝ
ፖለቲከኛ፤ ጌታ ለመሆን አገልጋይ መስሎ ይቀርባል፡፡
ቻርልስ ደጎል
እውነት በአብላጫ ድምፅ አይወሰንም፡፡
ዶግ ግዊን
ለችግሮቻቸው የቀድሞውን አስተዳደር ያልወቀሱ ብቸኛ ፕሬዚዳንት ጆርጅ ዋሺንግተን ናቸው፡፡
ያልታወቀ ፀሐፊ
ወግ አጥባቂ ማለት ምንም ነገር ለመጀመሪያ ጊዜ መሰራት የለበትም ብሎ የሚያምን ሰው ነው፡፡
አልፍሬድ ኢ.ዊጋም
የከተማዋን መክፈቻ ቁልፎች ለፖለቲከኛ ከመስጠት ይልቅ መቆለፊያዎቹን መቀየር ሳይሻል አይቀርም፡፡
ዶውግ ላርሰን
እጅግ በጣም ጥቂት ሴት ፖለቲከኞች ያሉበት ምክንያት ሁለት ፊት ላይ ሜክአፕ መቀባት በጣም አስቸጋሪ ስለሆነ ነው፡፡
ማዩሪን መርፊ
የቤተሰብ ሐረግህን ለማስጠናት ለምን ገንዘብ ትከፍላለህ፤ ፖለቲካ ውስጥ ግባና ተቀናቃኞችህ ያጠኑልሃል፡፡
ያልታወቀ ፀሃፊ
አንድ አሜሪካዊ ለዲሞክራሲ ለመዋጋት ውቅያኖስ ይሻገራል፤ ለብሄራዊ ምርጫ ድምፅ ለመስጠት ግን ጎዳና አይሻገርም፡፡
ቢል ቫውግሃን
ድምፅ መስጠት (ምርጫው) አይደለም ዲሞክራሲ የሚባለው፤ የድምፅ ቆጠራው ነው፡፡
ቶም ስቶፓርድ

            መቄዶንያ የአረጋውያንና የአዕምሮ ህሙማን መርጃ ማዕከል ባለፈው ሳምንት ቅዳሜ በማዕከሉ ባዘጋጀው የመስቀል በአል አከባበር ስነስርአት ላይ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተክርስቲያን የ100 ሺህ ብር የገንዘብ ድጋፍ አደረገች፡፡ በእለቱ የተገኙት የሰራተኛና ማህበራዊ ጉዳይ ቢሮ ልዩ ረዳት አቶ አሰፋ መብራቴ፤ ከማዕከሉ ጋር በጋራ ለመስራት ያላቸውን ፍቃደኝነት ገልፀዋል፡፡ በመስቀል አከባበር ስነስርአት ላይ የሃይማኖት አባቶችና የተለያዩ የመንግስት አካላት የተገኙ ሲሆን ዝግጅቱን በንግግር የጀመሩት የመቄዶንያ አማካሪ የሆኑት ዶክተር ብርሀኔ ጸጋዬ እና የድርጅቱ መስራችን ስራ አስኪያጅ አቶ ቢንያም በለጠ ማዕከሉ በአራት ማዕከላት 650 በላይ ለሚሆኑ ተረጂ ወገኖች ድጋፍ እየሰጠ መሆኑን ገልፀው ከመንግስት የጠየቀውን 30.000 ካሬ ሜትር ቦታ እንደተሰጠው፣ በቀጣይ አምስት አመታት ውስጥ የተረጂውን ቁጥር ወደ 10,000 /አስር ሺህ/ ለማሳደግ ዝግጅት መጀመሩን አስታውቀዋል፡፡
ማዕከሉም የጎበኙትና 100.000 ብር የለገሱት የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተክርስቲን ፓትሪያርክ ብፁህ ወቅዱስ አቡነ ማቲያስ ወእጨጌ ዘመንበረ ተክለሃይማኖት ብጹሃን ጳጳስ፣ ይህንን እርዳታ እንዲያደርጉ የረዳቸውን እግዚአብሔርን አመስግነው ማዕከሉ እያከናወነ ያለው ተግባር እግዚአብሔር የሚወደው መሆኑን የገለፁ ሲሆን እግዚአብሔር በፈቀደ ጊዜ ወደፊት በማስተባበርም ሆነ በገንዘብ እግዚአብሔር በሰጠን፣ አቅማችን በፈቀደ እንቀጥልበታለን ብለዋል፡፡
የሰራተኛና ማህበራዊ ጉዳይ ቢሮ ልዩ ረዳት አቶ አሰፋ መብራቴ፤ ይህ ተቋም ከሌሎች የተለየ እውቅናና ክብር እንድንሰጠው ያደረጉ ተግባሮችን እየሰራ ያለ ማዕከል ነው፡፡ ከማዕከሉ ጋር አብረን ለመስራት ፈቃደኛ መሆናችንን ማረጋገጥ እንወዳለን ያሉ ሲሆን፤ የወረዳ 9 ዋና ስራ አስፈፃሚ አቶ ሲሳይ በፈቃዱ በበኩላቸው፤ የሀገር ባለውለታ ለሆኑት አረጋውያን እየተደረገ ያለውን ድጋፍና እንቅስቃሴ በከፍተኛ ሁኔታ እናደንቀዋለን፤ ከዚህም ባሻገር እንደ አስተዳደር ልንተጋገዝ የሚገባ ጉዳይ ሲገኝ ተጋግዘን ለመስራት ዝግጁ ነን ብለዋል፡፡

ከ350 ሺ በላይ ተመዝጋቢዎች ይጠበቃሉ
ምዝገባው የሚካሄደው የስራ አጡን ቁጥር ለማወቅ ነው ተብሏል

        በአዲስ አበባ  ቤት ለቤት የሚካሄደው የስራ አጦች ምዝገባ አላማ በከተማዋ ያለውን የስራ አጥ ቁጥር ለማወቅ እንደሆነ የተገለጸ ሲሆን ከ350 ሺ በላይ ተመዝጋቢዎች ይጠበቃሉ ተብሏል፡፡ ወደ 9 ሚሊዮን ብር ገደማ በጀት ተይዞለት ከመስከረም 8 ቀን 2007 ዓ.ም ጀምሮ እየተካሄደ ያለው የስራ አጥነት ምዝገባ፤ በዋናነት በከተማዋ ምን ያህል ስራ አጥ አለ የሚለውን ለማወቅና በትክክለኛ መረጃ ላይ ተመስርቶ፣ የስራ እድሎችን ለማመቻቸት የታቀደ ፕሮጀክት እንደሆነ ተገልጿል፡፡
በከተማ አስተዳደሩ የሰራተኛና ማህበራዊ ጉዳይ ቢሮ፣ የኢንዱስትሪ ሰላምና የሙያ ደህንነት ዋና የስራ ሂደት መሪ አቶ ካሳ ስዩም ለአዲስ አድማስ በሰጡት ማብራሪያ፤ እንዲህ መሰሉ ምዝገባ ከዚህ ቀደምም በየጊዜው በከተማዋ እንደሚካሄድ አስታውሰው፣ የአለማቀፍ ሰራተኞች ድርጅት (ILO) ለአገራት ባስቀመጠው አቅጣጫ መሰረት፣ በከተማዋ ያለውን የስራ አጥነት ሁኔታ በተጠናከረ መረጃ የማደራጀት፣ የመተንተንና በትክክለኛ መረጃ ላይ ተንተርሶ መፍትሄ የመስጠት አካል ነው ብለዋል፡፡ የስራ አጥነትን ሁኔታ አጥንቶ የስራ እድሎችን ማመቻቸት የሰራተኛና ማህበራዊ ቢሮው አንዱ ኃላፊነት እንደሆነ የጠቆሙት ኃላፊው፤ ምዝገባው ከወር በኋላ ይጠናቀቃል ተብሎ እንደታቀደ ጠቁመዋል፡፡ ቤት ለቤት እየተካሄደ ያለው የስራ አጥነት ምዝገባ፣ ተመዝጋቢዎች በምን አይነት የስራ መስክ ላይ ቢሰማሩ ይመርጣሉ የሚለውን ያካተተ መሆኑን የጠቆሙት አቶ ካሳ፤ ምዝገባው ከተጠናቀቀ በኋላ የተሰበሰበው መረጃ ተተንትኖ፣ ተመዝጋቢዎች በሚፈልጉት የስራ መስክ ስልጠና ወስደው የሚሰማሩበት ሁኔታ ይመቻቻል ብለዋል፡፡
ቢሮው ስራና ሰራተኛን በነፃ የማገናኘት ኃላፊነቱን ለመወጣትም ራሱ ስራ አጦችንና ስራን ከማገናኘት ባለፈ ፍቃድ የተሰጣቸው ስራ አገናኝ ኤጀንሲዎች ስራ አጦችን ስራ በማስያዝ ተግባር እንዲሳተፉ ይደረጋል ብለዋል፡፡
ምዝገባው ከዚህ ቀደም ከተካሄዱት ለየት የሚያደርገው ጥናትን መሰረት አድርጎ የተለያዩ ማመላከቻዎችን መጠቀሙ እንደሆነ የገለፁት አቶ ካሣ፤ በከተማዋ ያሉ ስራ አጦች በየትኛው የስራ መስክ ነው የበለጠ መሰማራት የሚፈልጉት የሚለውን ለይቶ ለማወቅ ጠቀሜታ አለው ብለዋል፡፡ መረጃውን በመጠቀምም የተለያዩ የመንግስት እና የግል የሙያ ማሰልጠኛ ተቋማት የስልጠና መስካቸውን እንዲፈትሹ አጋዥ ይሆናል ሲሉ ኃላፊው አክለው ገልፀዋል፡፡
በምዝገባው ወቅት እድሜና የትምህርት ደረጃ የመሳሰሉትን ጨምሮ በትክክልም በአዲስ አበባ ነዋሪ ስለመሆናቸው መረጃዎች ይሰበሰባሉ ተብሏል፡፡ በአለማቀፍ የሰራተኞች ድርጅት መስፈርት መሰረት እድሜያቸው ከ14-18 ዓመት ያሉት በወጣት ስራ ፈላጊነት ይመዘገባሉ ያሉት ኃላፊው፤ በዚህ የእድሜ ክልል ላሉ በአቅማቸው ሊሰሩት የሚችሉት ስራ ይዘጋጅላቸዋል ብለዋል፡፡ አክለውም እድሜያቸው ከ60 በላይ የሆኑ በዚህ የምዝገባ ሂደት አይካተቱም ብለዋል - ኃላፊው፡፡ በየዓመቱ በርካታ የከተማዋ ስራ አጦች የስራ እድል እንዲያገኙ እየተደረገ መሆኑን የገለፁት አቶ ካሣ፤ በ2006 ዓ.ም ከ230 ሺህ በላይ ለሆኑ ስራ ፈላጊዎች የስራ እድል ተፈጥሯል ብለዋል፡፡ በዚህ የስራ አጦች ምዝገባ ፕሮጀክትም ከ350 ሺህ ያላነሱ ሰዎች ይመዘገባሉ ተብሎ የሚጠበቅ ሲሆን ምዝገባው የቤት ሰራተኞችን ጨምሮ ማንኛውም ተቀጥሮ የሚሰራና ገቢ የሚያገኝ ግለሰብን አይመለከትም ተብሏል፡፡
ስራ አጦችን ለመመዝገብ በቂ ዝግጅት ተደርጎ ወደ ስራ እንደተገባ የተናገሩት ኃላፊው፤ 734 ሰራተኞች በኮንትራት ተቀጥረው በከፍተኛ አማካሪነት፣ በሱፐርቫይዘርነት፣ በአስተባባሪነት እና በመረጃ አሰባሰቢነት እየተሳተፉ ነው ብለዋል፡፡ መረጃ ሰብሳቢዎችም በዲግሪ የተመረቁ እንደሆኑ አክለው ገልፀዋል፡፡
ከአዲስ አበባ በተጨማሪ በሁሉም የክልል ከተሞች በ2007 ዓ.ም በሃገሪቱ ምን ያህል ስራ አጦች አሉ የሚለውን በዘመናዊ መንገድ ለይቶ ለማወቅ ተመሳሳይ ምዝገባ ይደረጋል ተብሏል፡፡ ከዚህም ቀደም በሃገር አቀፍ ደረጃም ሆነ በአዲስ አበባ ከተማ ምን ያህል ስራ አጦች እንዳሉ አመላካች የሆነ በጥናት ላይ ተመስርቶ የተዘጋጀ መረጃ እንዳልነበረ ኃላፊው ተናግረዋል፡፡  

በገጣሚ እርቅይሁን በላይነህ የተፃፈው “እርቃንሽን ቅሪ” የተሰኘ የግጥም መድበል ሰሞኑን ለንባብ በቃ፡፡ በአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ የቴአትር ጥበባት መምህር የሆኑት ረዳት ፕሮፌሰር ሙሉጌታ ጀዋሬ በመፅሃፉ ጀርባ ላይ ባሰፈሩት አስተያየት፤ በመድበሉ የተካተቱት ግጥሞች ጠንካራ እንደሆኑ ጠቁመዋል፡፡
በወልቂጤ ዩኒቨርስቲ የቴአትር ጥበባት መምህር የሆኑት ጋዜጠኛ አስተዋይ መለስ በበኩላቸው፤ “ታሪክን የሚያወሱ ጥሩ ግጥሞች ናቸው” ሲሉ አድንቀዋል፡፡ በ132 ገፆች 77 ግጥሞችን ያካተተው መፅሀፉ፤ በ25 ብር ለሽያጭ ቀርቧል፡፡
ገጣሚው ከዚህ ቀደም “ያልተጠቡ ጡቶችን” የተሰኘ የአጫጭር ልብወለድ መድበልና  “የኢትዮጵያ ታሪክ ከኢማም አህመድ እስከ አጼ ቴዎድሮስ” የሚል የታሪክ መፅሃፍ ለንባብ ማብቃታቸው ይታወሳል፡፡

               በሩትገርስ ዩኒቨርሲቲና በሚቺጋን ዩኒቨርሲቲ በተካሄደ ጥናት፤ በትዳር ህይወት ውስጥ ከባልየው ይልቅ የሚስትየው ደስታ ለግንኙነታቸው ህልውና የበለጠ አስፈላጊ እንደሆነ ተረጋገጠ፡፡ ተመራማሪዎቹ በአማካይ ለ39 ዓመታት በትዳር የዘለቁ ጥንዶች ላይ ጥናት እንዳደረጉ ታውቋል፡፡ ጥንዶቹ የትዳር አጋሮቻቸው ያደንቋቸው፣ ይሞግቷቸው ወይም ያበሽቋቸው እንደሆነ የተጠየቁ ሲሆን በ24 ሰዓት ጊዜ ውስጥ በሚያከናውኗቸው የተወሰኑ ተግባራት - ለምሳሌ አስቤዛ መሸመት ወይም ቴሌቪዥን መመልከት … ምን ያህል ደስተኛ እንደሆኑ ተጠይቀዋል፡፡ አብዛኞቹ የጥናቱ ተሳታፊዎችም በትዳር ህይወታቸው ከፍተኛ እርካታ እንደሚሰማቸው ተናግረዋል፡፡ ሴቲቱ በባሏ ደስተኛ ከሆነች እሱም በአጠቃላይ ህይወቱ የበለጠ ደስተኛ ይሆናል - ስለትዳሩ የሚሰማው ስሜት ምንም ይሁን ምንም፤ ብሏል ጥናቱ፡፡
ከጥናት ፀሃፊዎቹ አንዷ የሆኑት ዲቦራህ ካር ለሩትገርስ እንደተናገሩት፤ “ሚስቲቱ በትዳሯ ስትረካ፣ ለባሏ የማታደርገው ነገር የለም፤ ይሄ ደግሞ በህይወቱ ላይ በጎ ተፅዕኖ ይፈጥራል ብዬ አስባለሁ፡፡ ወንዶች ስለትዳር ግንኙነታቸው ብዙም አያወሩም፤ ስለዚህም በትዳር ህይወታቸው ደስተኛ አለመሆናቸው ወደሚስቶቻቸው ላይጋባ ይችላል”
ሰውየው በትዳሩ ደስተኛ ካልሆነ፣ ሚስቱ ህይወቱን ብሩህ ለማድረግ የምታከናውናቸው ትናንሽ ነገሮች የደስታ እጦቱን ሊሸፍነው ይችላል፡፡ ወንዶች የጥናቱ ተሳታፊዎች ከሚስቶቻቸው ይልቅ ትዳራቸው መልካም ነው ብለው የሚያምኑ ሲሆን ትዳራቸው ከፍ ያለ ደረጃ ላይ እንደሆነ የሚያስቡ ተሳታፊዎች በሙሉ ግን በአብዛኛው የህይወት እርካታን የተጎናፀፉ ሆነው ተገኝተዋል - ያለምንም የፆታ ልዩነት፡፡

ተመራማሪዎቹ በጥናታቸው ያገኙት ሌላ ነገር ደግሞ ባሎች ሲታመሙ የሚስቶቻቸው ደስታ መጨመሩ ነው፡፡ ምክንያቱም ለባሎቻቸው እንክብካቤ የሚያደርጉት እነሱ በመሆናቸው ነው ተብሏል፡፡ በሌላ በኩል ሚስቶች ሲታመሙ ብዙ ጊዜ ለእርዳታ ፊታቸውን የሚያዞሩት ወደ ሴት ልጆቻቸው ነው፡፡ እናም የባሎች የደስታ መጠን ሳይለወጥ ባለበት ይቆያል፡፡ የትዳር ህይወት የጥራት ሁኔታና የደስታ መጠን ሰዎች ዕድሜያቸው እየገፋ ሲሄድ በጤናቸው ላይ ተፅዕኖ ያሳድራል፡፡ በዴቦራህ የጥናት ፅሁፍ  መሰረት፤ “ጥራት ያለው ትዳር አስፈላጊ ነው፤ ምክንያቱም በኋላ ዘመን ውጥረት ፈጣሪ ከሆኑ ጤና የሚያላሽቁ ተፅዕኖዎች መከላከያ ጋሻ ያጎናፅፋል፤ እንዲሁም ጥንዶች ጤናና ህክምናን የተመለከቱ አስቸጋሪ ውሳኔዎችን በቅጡ ለመወሰን ያግዛቸዋል፡፡”
በእናንተ የትዳር ግንኙነት በጥናቱ የተመለከተው ዓይነት ውጤት ገጥሟችኋል? ቢያንስ በግል ካስተዋልኩት፤ በትዳር ግንኙነታቸው ደስተኛ የሆኑ ሴቶች ለትዳር አጋሮቻቸው ተጨማሪ በጎ ነገር ለማድረግ ከመንገዳቸው እንደሚወጡ ተገንዝቤአለሁ፡፡ ይሄ ማለት ግን ወንዶች እንዲህ መሰሉን ነገር አያደርጉም ማለት አይደለም፡፡ ከዚህ ጥናት የምንረዳው አንድ ዋና ቁም ነገር፣ ሚስት ደስተኛ ስትሆን የትዳር ህይወት የሰመረ እንደሚሆን ነው፡፡ ንግስቲቷ ደስተኛ ስትሆን፣ መላው ቤተሰብ ደስተኛ ይሆናል እንደማለት!!

Monday, 06 October 2014 08:15

ማራኪ አንቀፅ

          ከአዋሳ እርሻ ኮሌጅ በዲፕሎማ ከተመረቅሁ በሁዋላ እዛው ከተማ 75 ዓመተምህረት ላይ በማውቀው ሰው እርዳታ ግብርና ሚኒስቴር ተቀጠርኩ፡፡ ‘አዲስ አበባ እንመድብሽ’ ቢሉኝም አልሄድም ነበር፡፡ አዲስአባን ጠላሁዋት፡፡ በቦዲ ሚሞሪ (የገላ ትውስታ ወይም የገላ ትዝታ) ይመስለኛል፡፡ ቦዲ ሚሞሪ (Body Memory) በአንጎል ውስጥ ብቻ ሳይሆን በሌላ የአካል ክፍል ውስጥም (በጡንቻ፣ በልፋጭ፣ በሞራ፣ በጉበት፣ በሳንባ ወዘተ) ትውስታ ሲከማች ማለት ነው፡፡ የፖለቲካ ጉዳዩ ከሽሮሜዳው አላዛር ጋር ተደርቦ አዲስአባን ስጠላ ትንሽ ልክ አይደለም፡፡ ባቡር ጣቢያ ምን አደረገኝ? በቅሎ ቤትና መካኒሳ ምን አደረጉኝ? እናቴ ለምን አዲስአባ እንደማልመጣ ስትጠይቀኝ  “እማመጃ ሙች መንግስት በእጣ ልመድብ እያለ አዋሳ ደረሰኝ፤ ገንዘብ ከፍዬ እንኳን የሚለውጠኝ አላገኘሁም፡፡ ምስክር ካስቸገረችሽ በደንብ ስቋቋም እወስዳታለሁ” አልኳት እማማ ‹ኸረ ለልጅቷ አይደለም፤ በሰራተኛ ከምታድግ ከእኔ ጋ ትሆናለች፡፡

ይሄን ደርግ የተባለ በጥባጭ ማን ላከብን እመቤቴ› ምናምን ምናምን፡፡ በልቤ የፈለግሽውን በይ እላለሁ፡፡ የአገራችን ምስክር መሃላ ነው፡፡ እንዋሽና እንምላለን፡፡ የማንምልበት የለም፡፡ ልብ ያልኩት እንዲህ ስገባበት ነው፡፡ በእግዚአብሔር እንምላለን፤ በሃይለስላሴ እንምላለን (ከንጉሠ ነገሥቱ የሚቀረው ጢማቸው ነው፣ እና ቀን ጠብቀንም ከተመቸን በጢማቸውም እንምላለን)፣ በመላእክት፣ በአባት፣ በእናት፣ በምንወደው ሰው፣ በደርጉ፣ በልባችን፣ በሳንባችን፣ በባላችንና በሚስታችን እንምላለን፡፡ በዚህ በዚህ ተለማምጄ ምናልባት በፋሲል እምላለሁ፤ በፋሲል ፔርሙስም እምላለሁ፡፡ ወደ አዋሳ ለመሄድ አንዳንድ እቃዎቼን በሻንጣ ስከት ያገኘሁዋቸውን የማርኪሲስት መፅሀፍት ለማድቤት እሳት ወረወርኩ፡፡ እስር ቤት ሙላት የሰጠኝን ያማረች ቅል እንዳትሰበርብኝ በጥንቃቄ በወረቀትና በላስቲክ ጠቅልዬ በልብሶቼ መሃል ወሸቅሁዋት፡፡ ድሮ አበባና ተክሎችን ከሰበሰብኩባቸው ሶስት አልበሞቼ አንዱን ብቻ አገኘሁ፡፡

ታስሬ ከተወሰድኩ በኋላ በበነጋታው ፈታሾች እኔን የሚወነጅሉበት ጸረ-አብዮት ወረቀት ሊያገኙ ሲበረብሩ እንደነበር ተነግሮኛል፡፡ የቀሩትን በርባሪዎቹ እንደወሰዱአቸው አውቃለሁ፡፡ ቢያበሳጭም ምን ይደረጋል? “ምን አውቃለሁ የሆነ ወረቀት ሰብስበው ሄዱ” አለች እማማ፤ ቀኑ ሲያልፍ፡፡
አላለፈም፡፡ በልጅነቴ የለፋሁበት ሲጠፋ ሃዘን አይገባኝም አሉ? ሃዘን ካለ የአልበሞቼ ትዝታ አለ ማለት ነው፡፡ ሁሉም አልበሞቼ ገና እኔ ውስጥ አሉ፡፡ ትንሽ ተቀምጬ ከትውስታዬ ሊጠፋ የጀመሩ አትክልቶችን እየገለጥኩ አየሁ፡፡ የመፅሀፉ ጠረን መስከረም ወር ውስጥ እንደሚያጋጥም የእንጦጦ ሸለቆ ነው፡፡ መጨረሻው ገፅ ላይ አንድ ጠጅ ሳር አገኘሁ፡፡ ገና በጣቴ ስነካካው ፈራረሰ፡፡ መደርደሪያዬ ላይ ደሞ ምናልባት ከሰባት አመታት በፊት አላዛር ለልደት ቀኔ የሰጠኝን አንድ ዳልሜሽያን የውሻ አሻንጉሊት አገኘሁ፡፡ ወደ ግድግዳ ገፋ ተደርጋለች፡፡ አቧራ ለብሳለች፡፡ በአዲስነቷ በጥቁር ነጠብጣቦች የተሸፈነች በረዶ ነጭ ነበረች፡፡ አይኖቿ ጥቁር ሆነው በዙሪያቸውን አረንጓዴ ናቸው፡፡ አፍንጫዋ ጥቁር ነው፡፡ ጅራተ ጎራዳ ናት፡፡ አልጋዬ ላይ በጀርባዬ ስሆን ሳታቋርጥ ታየኝ ነበር፡፡ አስተያየቷ ያባባል፡፡ ቆሻሻዋን አራግፌ ሻንጣዬ ውስጥ ከተተትኳት፡፡
አቶ አባይ አዋሳ አደርሳታለሁ ስላሉ ሳሎን ተቀምጬ እሳቸውን ስጠብቅ ቆይቼ፣ ሰልችቶኝ መኝታ ቤት ስገባ፣ እማማ ሻንጣዬን ስትበረብር አገኘሁዋት፡፡ በቀኝ እጅዋ ዳልሜሽያን አሻንጉሊቷን ይዛለች፤ ቀና ብላ በማዘን አየችኝና ምንም ሳትናገር እነበረችበት አመቻችታ አስቀመጠቻች፡፡ አፍሬ ወደ ሳሎን ተመለስኩ፡፡ አለሁበት መጥታ ምንም ነገር እንዳልሆነ፡፡
“አባይ የት ጠፋ? እያረጀ ሲሄድ ቀጠሮ መርሳት ጀመረ?” አለች፡፡ አልመለስኩላትም፡፡
አጠገቧ እግሮቿ ስር በጉዞዬ አውቶቡስ ውስጥ የምበላቸው ብርቱካኖች ሙዞች ተደጋግፈው ተቀምጠዋል፡፡ ብርቱካኑ ቅጠልያ ቀለሙ አልተወውም፡፡ ሎሚ አስተኔ ቆምጣጣ ሳይሆን አይቀርም፡፡ ፍራፍሬ ኮርፖሬሽን ቤመንገዱ ድንኩዋን ተክሎ ኪሎው በሁለት ብር ካምሳ ከሚሸጠው ከእማማ ገዝታ ነው፡፡ ከነዚህ ጎን ደሞ ገና አረንጓዴነቱ ያለቀቀው ጥሬ ሙዝ አለ፡፡ እማማ ከመስሪያቤቷ ስትወጣ፣ የስራ ጓደኛዋ ልጅሽን ደህና ግቢ በይልኝ ብላ የላከችልኝ ነው፡፡ ከሴትዬዋ አልቀራረብም፡፡ ሙዞቹ ጥሬ ከመሆናቸው የተነሳ እያንዳንዳቸው ሁለት ሁለት ጠንከራ ሰረሰሮች አሉዋቸው፡፡ ስድስቱም አንድ አንጓ ላይ እንደ ደራጎን ጥርስ ተደርድረዋል፡፡
እማማ የላስቲክ ቀረጢቱን በእግሯ እየነካካች ታስባለች፤ ስለ እኔ ጉዞና ሰፈር ስለመቀየር ይሁን ስለ አባይ እንጃ፡፡ እኔ መሄዴ ነው፡፡ እማማ ብቻዋን መኖር የምትችል አይመስለኝም፡፡ ከአባይ ጋር ለምን እንደማይጋቡ አይገባኝም፡፡ አሻንጉሊቴን ባታይብኝ ኖሮ ትዳር ስለመመስረት እጠይቃት ነበር፡፡ ግን፤“አንቺስ አሻንጉሊት ከመሰብሰብ አላዛርን ጠበቅ አታደርጊም ነበር” ብትለኝስ ብዬ ተውኩት፡፡ በየቀኑ በደም ስሬ፣ በልቦናዬ ደካማ የሚያደርገኝን ነገር የምሰበስብ ይመስለኛል፡፡----
(ከደራሲ አዳም ረታ
መረቅ የተሰኘ አዲስ ረዥም ልብወለድ
መጽሃፍ ውስጥ የተቀነጨበ፤2007 ዓ.ም)

Monday, 06 October 2014 08:13

እንቆቅልሽ?

ወደታች የሚወርድ፣ ወደላይ ግን የማይወጣ?
በወጣትነቴ ረዥም ነኝ፡፡ ሳረጅ አጭር እሆናለሁ፡፡ ማን ነኝ?
የሜሪ አባት አምስት ሴት ልጆች     አሏቸው፡፡ ናና፣ ኔኔ፣ ኒኒ፣ ኖኖ ይባላሉ፡፡ የአምስተኛዋ ልጃቸው     ስም ማነው?
ካለኝ ለሰው አላካፍለውም፡፡ ለሰውካካፈልኩት አይኖረኝም፡፡ ምንድነው?
ሰውየው ከባድ መኪና እየነዳ ነው፡፡ የፊት መብራት አላበራም፡፡ ጨረቃም አልወጣችም፡፡
ከፊት ለፊቱ አንዲት ሴት መንገድ ታቋርጣለች፡፡እንዴት አያት?

====================


መልስ
ዝናብ
ሻማ
ሜሪ
ምስጢር
ብሩህና ፀሐያማ ቀን ነበር

(የወላይታ ምሳሌያዊ አነጋገር)

ከዕለታት አንድ ቀን አንዲት ዶሮና አንድ አውራ ዶሮ ወደ አንድ ፍሬ ወደ ሚገኝበት ተራራ ይወጣሉ፡፡ አንድ ስምምነት እንዲያደርጉም መነጋገር ጀመሩ፡-
አውራ ዶሮ ---------- እመት ዶሮ
እመት ዶሮ ---------- አቤት አያ አውራ ዶሮ
አውራ ዶሮ ------- አንድ ነገር እንስማማ
እመት ዶሮ -------- ምን አሰብክ ወዳጄ?
አውራ ዶሮ -------- ምንም ዓይነት ፍሬ ብናገኝ አንዳችን ላንዳችን እናካፍል
እመት ዶሮ ----- በሃሳቡ እስማማለሁ፡፡ ድንቅ መርህ ነው!
በዚህ ስምምነት ፀንተው ያን ተራራ ተያያዙት፡፡ ከሰዓታት በኋላ እመት ዶሮ አንድ ትልቅ ፍሬ አገኘች፡፡ ግን ስለማግኘቷ አንዲትም ቃል ትንፍሽ ሳትል መንገድ ቀጠለች፡፡ አንድ አሳቻ ቦታ ስትደርስ፣ ዘወር ብላ ፍሬውን ልትበላ ሞከረች፡፡ ሆኖም ፍሬው በጣም ትልቅ በመሆኑ አልዋጥ አላት፡፡ አንቆ የሚገላት መስሎ ስለተሰማት፣ በጣም ደነገጠች
“አያ አውራ ዶሮ! አያ አውራ ዶሮ!” ስትል ጮኸች፡፡
አውራ ዶሮም፤ “ምነው? እመት ዶሮ ምን ሆንሽ?” አላት፤ ካለበት ሆኖ፡፡
“እባክህ ትን ብሎኝ ልሞት ነውና ውሃ ፈልገህ አምጣልኝ”
አውራ ዶሮው በአቅራቢያው ወደሚገኝ አንድ የውሃ ጉድጓድ ሄዶ፤ “ጉድጓድ ሆይ! እባክህ እመት ዶሮ ልትሞትብኝ ነውና ትንሽ ውሃ ስጠኝ?” ሲል ጠየቀው፡፡
ጉድጓዱም፤ “መስጠት እሰጥሃለሁ፡፡ ግን በመጀመሪያ ከዕለታት አንድ ቀን የአፌ መሸፈኛ የሆነውን ቀይ ሀር ጨርቅ፣ እመት ዶሮ ሰርቃ ወስዳብኛለችና ከጌታዋ ቤት ሄደህ አምጣልኝ” አለው፡፡
አውራ ዶሮው አሁንም የዶሮ ጌታው ዘንድ እየበረረ ሄዶ፤
“ጌታዬ፤ እመት ዶሮ በውሃ እጦት ልትሞት ቢሆን፤ ጉድጓድን ውሃ ስጠኝ ልለው ሄድኩ፡፡ እሱም ወደ ጌታዋ ዘንድ ሄደህ የሰረቀችኝን ሀር አምጣ አለኝ፡፡ እባክዎ ሀሩን ይስጡኝና ውሃ ላግኝላት?” ሲል ጠየቀው፡፡
ጌትዬውም፤ “በመጀመሪያ ከቤት ሰርቃ የወሰደችውንና ለዶሮ ጠባቂው የሰጠችውን ሰዓት አስመልስልኝ” አለው፡፡
አውራ ዶሮ ሲበር ሄዶ ዶሮ ጠባቂውን ለመነውና ሰዓቱን አስመልሶ ለጌትዬው መለሰ፡፡ ቀዩን ሀር ተቀብሎ ለጉድጓዱ ሰጠ፡፡ ውሃውንም ከጉድጓዱ ወስዶ ለዶሮዋ ሊሰጥ ወደ ተራራው ወጣ፡፡ እዚያ ሲደርስ ግን እመት ዶሮ ለአንዴም ለሁሌም አሸልባለች፡፡
                              *           *         *
አበው “ብቻውን የበላ ብቻውን ይሞታል” ይላሉ፡፡ አንድም ደግሞ “ሥራ ለሰሪው እሾህ ለአጣሪው” ይላሉ፡፡ የሰራነው ሥራ እስከ እለተ ሞታችን ድረስ ይከተለናል፡፡ እያንዳንዷ ዱካችን የማታ ማታ ተከትላ ታጋልጠናለች፡፡ የሙስና የመጨረሻ ፍፃሜ እንደዶሮይቱ በተያያዘ ጥፋት ዋጋ መክፈል ነው፡፡ Domino effect እንዲሉ ፈረንጆች፡፡ አይታወቅብኝ በሚል በአልጠግብ ባይነት በአሳቻ ቦታና ሰዓት የመነተፍነው የህዝብ ንብረትና ንዋይ፣ አንድ ቀን ክፉ ቦታ ላይ እንደሚጥለን እንገንዘብ፡፡ ቃልን ማፍረስ፣ የሀገርን ሀብት መበዝበዝ፣ የሀገርን ክብር ማዋረድ፤ ሁሉም ዓይነት ሙስናዎች የማታ ማታ ያስጠይቃሉ፡፡
የተጠርጣሪዎች መብዛት፣ ከስራ መባረሮች፣ የጥርጣሬና ፍርሃት መንገስ፣ ከተሾሙበት ስልጣን መባረር መብዛት ወዘተ ሁሉም የሙስና መገለጫዎች ናቸው፡፡ ስለሆነም የተገለጠ ዐይን ይፈልጋሉ፡፡ ይህንን ለማስተካከል አንጋረ ፈላስፋ የሚለንን ማዳመጥ መልካም ነው፡-
“ንጉሥ ሦስት ነገሮችን ገንዘብ ማድረግ ይገባዋል፡-”
1ኛ/ ዐዋቂዎቹን አክብሮ መያዝ
2ኛ/ ለተቸገሩት መስጠትና በማናቸውም መርዳት
3ኛ/ ህዝቡን በቅንነትና በርህራሄ ማስተዳደር፡፡”
    ቀጥሎም እንዲህ ይለናል፡-
“ብልህ ዐዋቂ ሰው፣ አንደበቱ የልቡ አማካሪ ነው፡፡ መናገር ሲያምረው አስቀድሞ በልቡ ያወጣ ያወርድና፣ ለመናገር መንገድ ሲያገኝ ይናገራል፣ ባያገኝ ግን ዝም ይላል፡፡ ቁም ነገሩ ይኸው በጎውንና ክፉውን ለይቶ መናገር ነው” ስለዚህም ነው የሙስናን ጣራ መንካት ደጋግመን ስንናገር የከረምነው፡፡ ዛሬም ያንኑ የሙስና መንገድ የሚከተሉ አያሌ ናቸው፡፡ የሌሎች መጠርጠር፣ የሌሎች መታሰር የማያስደነግጣቸው አያሌ ናቸው፡፡ የሚሰነዘረው በትር የማቀፍ ያህል ፈገግ የሚያሰኛቸው በሺዎች የሚቆጠሩ ናቸው፡፡
“ጉርሻ የለመደች ሴት በጥፊ ሊመቷት እጅ ሲያነሱ አፏን ትከፍታለች፡፡” የሚለው የወላይታ ተረት የሚነግረን ይሄንኑ ነው፡፡
ኢድ ሙባረክ!

  • በዋሺንግተን የኢትዮጵያ ኤምባሲ መሳሪያ የተኮሰው

 የፀጥታ ሰራተኛ ወደ ኢትዮጵያ ተመለሰ

በሳምንቱ መጀመሪያ ዋሺንግተን ዲሲ በሚገኘው የኢትዮጵያ ኤምባሲ ላይ በዳያስፖራ ተቃዋሚዎች የተደረገውን ጥሰት ተከትሎ፣ ባለፈው ረቡዕም በስዊድን የኢትዮጵያ ኤምባሲ ላይ በተቃዋሚዎች ተመሳሳይ የጥሰት ሙከራ መደረጉን ምንጮቻችን ለአዲስ አድማስ ገለፁ፡፡ በስዊድን ስቶክሆልም በሚገኘው የኢትዮጵያ ኤምባሲ ላይ ባለፈው ረቡዕ የዳያስፖራ ተቃዋሚዎች ተመሳሳይ የጥሰት ድርጊት ለመፈፀምና በስዊድን የኢትዮጵያ አምባሳደር ወይንሸት አሰፋ ላይ ለሁለተኛ ጊዜ ጥቃት ለማድረስ እንደሞከሩ የጠቆሙ ምንጮች፤ የፀጥታ ሃይሎች ደርሰው ሙከራውን እንዳከሸፉት ገልፀዋል፡፡
በአሜሪካ የኢትዮጵያ ኤምባሲን ቅጥር ግቢ  ጥሰው ከገቡ የዳያስፖራ ተቃዋሚዎች ጋር በተፈጠረ አተካሮ መሳሪያ ወደ ላይ የተኮሰው የኤምባሲው የፀጥታ ሰራተኛ ያለመከሰስ መብቱን ተጠቅሞ ወደ ኢትዮጵያ መመለሱን የአሜሪካ የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር የፕሬስ ኃላፊ ጄን ሳኪ አስታወቁ፡፡
ባለፈው ሰኞ  የተወሰኑ ያለ የዳያስፖራ ተቃዋሚዎች የኢትዮጵያ ኤምባሲ ቅጥር ግቢ ጥሰው መግባታቸውን ተከትሎ በተፈጠረ አምባጓሮ ሰለሞን ገብረስላሴ (በቅፅል ስሙ ወዲ ወይን) የተባለው የኤምባሲው የፀጥታ ሰራተኛ መሳሪያ በመተኮሱ፣ የአሜሪካ የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር የግለሰቡ ያለመከሰስ መብት ተነስቶ ጉዳዩ በአሜሪካ ፍርድ ቤት እንዲታይ ጥያቄ ያቀረበ ሲሆን ጥያቄው በኢትዮጵያ መንግስት በኩል ተቀባይነት ባለማግኘቱ ወደ አገሩ እንዲመለስ ተደርጓል ተብሏል፡፡ በተመሳሳይ ምክንያት ከአሜሪካ የወጣ ማንኛውም ዲፕሎማት ወደ አሜሪካ መመለስ የሚችለው ክሱ በፍርድ ቤት እንዲታይ ብቻ ነው፡፡
በዋሺንግተን ዲሲ በሚገኘው የኢትዮጵያ ኤምባሲ ላይ በዳያስፖራ ተቃዋሚዎች የተፈጸመውን ጥሰት እንዲሁም የኤምባሲውን ደህንነት ጉዳይ በተመለከተ በአዲስ አበባ ለሚገኘው የአሜሪካ ኤምባሲ ላቀረብነው ጥያቄ፣ የኤምባሲው የኢንፎርሜሽንና ፕሬስ ኃላፊ ካትሪን ዲዮፕ በሰጡት ምላሽ፤ “በኢትዮጵያ ኤምባሲ ላይ በግለሰቦች በተፈፀመው ድርጊት በጣም አዝነናል፤ ነገር ግን ጉዳዩ በምርመራ ላይ በመሆኑ አስተየያየት መስጠት አንችልም፣ በዋሽንግተን ዲሲና በሌሎች ግዛቶች ለሚገኙ ኤምባሲዎች ደህንነት አሜሪካ ትኩረት እንደምትሰጥ እናረጋግጣለን” ብለዋል፡፡ የኢትዮጵያ መንግስት በአዲስ አበባ ለሚገኘው የአሜሪካ ኤምባሲ የሚያደርገውን ጥበቃ በእጅጉ እንደሚያደንቁም ኃላፊዋ ተናግረዋል፡፡
ከትናንት በስቲያ የውጪ ጉዳይ ሚኒስቴር ቃል አቀባይ አምባሳደር ዲና ሙፍቲ በፅህፈት ቤታቸው ለጋዜጠኞች በሰጡት መግለጫ፤ በአሜሪካ የኢትዮጵያ ኤምባሲ መጣስንና መሳሪያ ስለተኮሰው የሚኒስቴር መስሪያ ቤቱ ባልደረባ ተጠይቀው፣ “በአሁኑ ወቅት ጉዳዩን አስመልክቶ ሙሉ ስዕል የለኝም” በማለት ምላሽ ሰጥተዋል፡፡ በጉዳዩ ላይ አስተያየት እንዲሰጡን ሌሎች የውጪ ጉዳይ ሚኒስትር ሃላፊዎችን ለማግኘት ያደረግነው ተደጋጋሚ ሙከራ አልተሳካም፡፡  በሰሞነኛ አበይት ጉዳዮች ላይ ትንታኔ የሚሰጠው የሚኒስቴር መስሪያ ቤቱ ድረ ገፅም ማተሚያ ቤት እስከገባንበት ሰዓት ድረስ በጉዳዩ ላይ ያለው ነገር የለም፡፡