Administrator

Administrator

አርቲስት ተስፋዬ ማሞ ሁለገብ የኪነጥበብ ሰው ነው፡፡ በማስታወቂያ ሥራዎቹ ይታወቃል፡፡ ደራሲና የፊልም ባለሙያም ነው፡፡ የሬዲዮ ፕሮግራም አዘጋጅም ነው፤ ተስፋዬ ማሞ፡፡ የአዲስ አድማስ ጋዜጣ 25ኛ ዓመትን አስመልክተን ቃለምልልስ አድርገንለታል፡፡
ከአዲስ አድማስ ጋር እንዴት እንደተገናኘና እንደተዋወቀ ያወጋናል፡፡ ጋዜጣው ብዙ ዋጋ እንደተከፈለበትም ይናገራል፡፡ ሁሉንም ከባለቤቱ አንደበት እነሆ፡-

 ለመሆኑ ተስፋዬ እና አዲስ አድማስ ጋዜጣ እንደምን ተገናኙ?

ከአዲስ አድማስ ጋር የተገናኘነው ገና ሳትወለድ በፊት ነው። መጀመሪያ የተዋወቅነው ከአሰፋ ጎሳዬ ጋር ነው። አሰፋ የዓለምን ካርታ በአማርኛ ከሰራ በኋላ ማስታወቂያዎችን ይሰራ ነበር። ለፒኤስአይ፣ ለዲኬቲ ኢትዮጵያ የሚሰራቸው ማስታወቂያዎች ነበሩ። እናም፣ እነዚህን ማስታወቂያዎች እኔ ነበርኩ በድምጽ የማነብለት። በዚህ ምክንያት ከአሰፋ ጋር የወንድም ያህል ጓደኛሞች ነበርን። የማንነጣጠል -- አብረን የምንበላ፣ አብረን የምንጠጣ፣ አብረን የምንዞር፣ አብረን የምንውል -- ጓደኛሞች፡፡ እና፣ አሰፋ ህልሙን ሲያልም ጀምሮ አውቃለሁ፤ አዲስ አድማስን። ምክንያቱም አዲስ አድማስ ከመምጣቱ ከዓመታት በፊት -- ጋዜጣው እስከሚወለድበት፣ እስከ 1992 ድረስ ጽሁፎችን ይሰበስብ ነበር። አሪፍ ጽሁፎችን ሲያገኝ ይሰበስባል፡፡ አዲስ አድማስ ላይ ይወጡ የነበሩ የባሴ ሃብቴ ጽሁፎች በሙሉ በዚያ ጊዜ የተሰበሰቡ ናቸው። ጥሩ ጽሁፍ፣ ጥሩ ሃሳብ ካገኘ አንድ ቀን አንድ ነገር “ሊሆን ይችላል” እያለ ይሰበስብ ነበር፡፡ ”አዲስ አድማስ” ተብሎ ስም አይውጣለት እንጂ የሕትመት ስራ እንደሚሰራ ያውቅ ነበር፤ አሰፋ። በዚህም ምክንያት ጽሁፎችን ሲያከማች ነው የቆየው፡፡ እየተረጎምን ጽሁፎችን እናስቀምጥ ነበር። እኔ ዘንድ የ“ሪደርስ ዳይጀስት” በጣም ብዙ ቅጾች ነበሩ፡፡ “ጉድ ሃውስ ኪፒንግ” የሚባል መጽሔቶችም ነበሩኝ። እነዚያን መጽሔቶች ይዘን፣ በእነርሱ ላይ ተመስርተን ሃሳቦችን እንከትብ ነበር። የዓመታት ድምር ሃሳቦች ውጤት ነው አዲስ አድማስን እንዲወለድ ያደረገው። አዲስ አድማስ ከአድማስ አድቨርታይዚንግ ነው የወጣው፤ የአሰፋ መሰረት አድማስ ነውና፣ “አዲስ አድማስ ጋዜጣ” የሚባል ተመሰረተ።
መንገዱ ግን እንዲህ እንደማወራልህ አልነበረም፤ በጣም ከባድና በጣም አስቸጋሪ ነበር፡፡ እንግዲህ ከ1990 በፊት በነበሩት ጊዜያት፣ ገና ከጽንስ በፊት የሃሳብ መብላላቶች ውስጥ ነው አብረን የነበርነው። እንዲያውም የማልረሳው አሰፋ ወሎን በጣም ነበር የሚወደው፤ የወሎን ትውፊቶች፣ ታሪኮቹን በጣም ስለሚወድ፤ እኔም አወራው ስለነበር፤ “ሁኔታዎች ቢመቻቹ እያንዳንዱ የወሎ አውራጃ ውስጥ አንድ አንድ ወር ተቀምጠህ ታሪኮች ተጽፈው ቢመጡ” ይለኝ ነበር፡፡ ምክንያቱም ወሎ በጣም ብዙ ትውፊትና በጣም ብዙ ታሪክ ያለበት አገር ስለሆነ፣ እዚያ ድረስ አሰፋ ለጽሁፍ ክምችት በጣም ያስብ ነበር።
እንግዲህ ይህ ሁሉ የጽሁፍ ክምችት ተሰበሰበ፣ አጠቃላይ ሂደቶች ተከናወኑና ወደ ሕትመት ሊገባ ነው። የሕትመት ቅድመ ዝግጅቱ ምን ይመስል ነበር?
የአድማስ አድቨርታይዚንግ ቢሮ ራስ ሆቴል ፊት ለፊት ነው የነበረው። በዚያ ቢሮ የቅድመ ዝግጅት ስራዎች ይሰሩበት ነበር፡፡ አዲስ አድማስ እንደ ጋዜጣ ስም ወጥቶለት፣ ሥራ ለማስጀመር ሲታሰብ ግን ንግድ ማተሚያ ቤት አካባቢ፣ አንድ ቤት ለአጭር ጊዜ ተከራየ፡፡ የመጀመሪያው የአዲስ አድማስ የሥራ ቦታ እዚያ ነው የነበረው። ብዙ ሠራተኛ አልነበረውም።
ምን ያህል ሠራተኞች ነበሩ?
አሰፋ ራሱ፣ ሰለሞን ጎሳዬ፣ ሰዓሊው መስፍን ሃብተማርያም፣ የውብዳር የምትባል ጸሐፊ... እና ጌታቸው አበራ ነበረ። በተረፈ አዳዲስ -- ገና ብቅ ብቅ የሚሉ ልጆች ናቸው የነበሩት። እነ ነቢይ መኮንን ያኔ አልመጡም ነበር። ነቢይ በኋላ እዚህኛው ቢሮ ከተቀየረ በኋላ ነው የመጣው። የቅድመ ዝግጅትና የመጀመሪያዎቹ የአዲስ አድማስ ሕትመት የጀመረው እዚህ ንግድ ማተሚያ ቤት አካባቢ የነበረው ቢሮ ነው። እርሱ ቦታውም፣ ሁኔታውም ጥሩ ስላልነበር -- ሦስት ወይም አራት ወር መቆየቱን እርግጠኛ አይደለሁም -- ያን ያህል ጊዜ አልቆየም። ለአጭር ጊዜ ነው የቆየው። እርሱ ተለቅቆ ለም ሆቴል አካባቢ አንድ ሌላ ቢሮ ውስጥ ተገባ። ሲጀመር፣ እንደ ኮቴጅ (ጎጆ) ኢንዱስትሪ በቤተሰብ፣ በጓደኛና በዙሪያው ባለን ሰዎች ነው የተጀመረው። እኔ ሁለት ዓምዶችን ይዤ ነበር፤ “ካሰብነው ይገርማል” የሚል እና አንድ ሌላ “በሳምንቱ ውስጥ ምን አለ? ምን ትጠብቃላችሁ?” የሚል። በኋላ እነ ነቢይ መኮንን መጡ። እነ ሰለሞን ገብረ እግዚአብሔር መጡ፡፡ እነ ሰለሞን አበበ ቸኮል (ሰአቸ) መጡ። ከዚያ እያደገ ሄደ።
አዲስ አድማስ ጋዜጣ መታተም እንደጀመረ በቀላሉ አልተለመደም፤ በርካታ ኮፒዎች ከገበያ ይመለሱ ነበር። ይታተማል፤ ተመልሶ ይመጣል። ለማስለመድ የነበረው መከራ ቀላል አልነበረም፡፡፡ አንዳንድ ሰዎች፤ “አሰፋ፣ ይህ ብርቱካናማ ቀለም ይቀየር፣ ሰውን የሚገፋብን ቀለሙ ነው” ይሉት ነበር። አሰፋ ደግሞ፤ “የአባቴን ቤት እስከመሸጥ እሄዳለሁ እንጂ ይህንን ሎጎ አልቀይረውም። ከአቋሜ፣ ከያዝኩት ስታንዳርድ አንዲት ኢንች ዝቅ አልልም” ይል ነበር። ምክንያቱም ያኔ ጊዜው የገተር ፕሬስ (Gutter Press) -- የእነ”ጎዳናው” -- ጊዜ ነው የነበረው። አሁን ፌስቡክ ላይ እንዳለው፣ መንችፎ የመሮጥ ዓይነት ነገር የለም? በብዛት የሚነበቡት እንደእነርሱ ዓይነት ጋዜጦች ነበሩ። ሆሮስኮፕ ያላቸው፣ የፈረንጅ ታሪኮች ተተርጉመው የሚወጡባቸው ጋዜጦች ነበሩ የተለመዱት። በዚያ መሃል ቁምነገሮችና ዕውቀት የሚያስጨብጥ፣ ፍልስፍናን የተሸከሙ ሃሳቦች ያሉት አዲስ አድማስ ጋዜጣ መጣ። ያልተለመደ ነበር፤ በዚህም የተነሳ በነጻ እስከመበተን ተደርሷል፤ ለማስለመድ፡፡ ምሁሩና የማንበብ ፍላጎት ያለው ሰው ዘንድ እንዲደርስ በጣም ብዙ ተሰርቷል፤ በሸክም ወጥቶ በሸክም እየተመለሰ፣ አዟሪዎች እጅ ላይ ይቆይ ነበር፡፡ ደግነቱ አዲስ አድማስ ሳምንትም፣ ወርም፣ ዓመትም ቆይተህ ብታነብበው፣ አያልፍበትም፡፡ ሁሌም የሚነበብ ጋዜጣ ነው፡፡
እንዲህ እንዲህ እያለ ቀስ በቀስ አዲስ አድማስ በየሳምንቱ ቅዳሜ በናፍቆትና በጉጉት የሚጠበቅ ጋዜጣ ለመሆን በቃ። ግን ብዙ ዋጋ ተከፍሎበታል፤ ዝም ብዬ ቀለል አድርጌ እንደምነግርህ አይደለም፡፡ ያ ሁሉ ተለፍቶ፣ ያ ሁሉ ጽሁፍ ተጠራቅሞ የሚሰራው ስራ እስኪለመድ እየተመለሰ ሲመጣ ምን ያህል አስቸጋሪ እንደነበረ መገመት ይቻላል፡፡ ...persistence የሚባለውን ነገር እኔ ያየሁት ያኔ ነው፡፡ አሰፋ በዚህ በጣም የሚገርም ሰው ነበር፡፡ “የአባቴ ቤት ካስፈለገ ይሸጣል እንጂ አላፈገፍግም” የሚል አቋም ስለነበረው፣ በአቋሙ ጸንቶ ከደረጃው ዝቅ እንዳይል በደረጃው እንዲያድግ አድርጎ፣ በዙሪያውም ሌሎች ብዙ ሰዎች እንዲሰሩ በማድረጉ ምክንያት ነው ለተወዳጅነት የበቃው።
ከመጀመሪያው ዕትም በአዕምሮህ ውስጥ ጎላ ብሎ የሚታወስህ ዓምድ የትኛው ነው?
ጋዜጣው በቂና ሙሉ ዝግጅት የተደረገበት በመሆኑ ምሉዕ ነበር ማለት ይቻላል፡፡ እያንዳንዱ ዓምድ ራሱን ችሎ የቆመ ነበር፤ አንደኛው ከሌላኛው ጋር የሚነጻጸር አልነበረም፡፡ ሁሉም በራሱ ሙሉ ነው፡፡ ከሳምንት ሳምንት የሚነበብ ጋዜጣ ነው የነበረው፡፡ የካርቱን ምስሎቹ፣ የገጽ ቅንብሩ፣ መልኩ ሁሉ የሚያምር ጋዜጣ ነው። በዝግጅት በአቀራረብና በይዘት፣ በቅንብርም ደረጃ የተስተካከለና የተሟላ እንዲሆን ብዙ ጥረት የተደረገበት ጋዜጣ ነው፡፡ ስለዚህ የምትጥላቸው ጽሁፎች አልነበሩም።
በዚህ መልኩ የጀመረው አዲስ አድማስ የዘለቀበትን መንገድ እንደ አንድ አብሮ እንደነበረና ኋላም በቅርብ ርቀት ሆኖ እንደሚከታተል ሰው የጋዜጣውን ዕድገት እንደምን ነበር የምትገመግመው?
እኔ ረዥሙን ጊዜ ከጋዜጣው ጋር አብሬ ነበርኩ፤ አልጻፍና ወደ ራሴ ስራ አልምጣ እንጂ። ምክንያቱም ከጅማሮ አንስተህ አብረህ የነበርክበት ስራ ወይም አንድ ልጅ ተወልዶ ሲያድግ ዓይንህ መከተሉ አይቀርም። ስለዚህ በተመሳሳይ ሁኔታ አዲስ አድማስን እከተል ነበር። አዲስ አድማስ እንደነገርኩህ ሲጀመር በጣም ከፍ ተደርጎ ነው የተጀመረው፡፡ ስለዚህም ሰዎች አንብበው የማይጥሉት ጋዜጣ ነው የሆነው፡፡ ብዙ ቦታዎች ላይ ክበቦች፣ ትናንሽ የጓደኛሞች ስብስብ ነበሩ፤ አዲስ አድማስን ቅዳሜ ቅዳሜ ጠብቀው ቁጭ ብለው አንብበው የሚወያዩ። አዲስ አድማስ ጋዜጣ የመወያያ፣ የመነጋገሪያ አጀንዳ ነው የነበረው፡፡ ከዚያም በናፍቆት የሚጠበቅ ጋዜጣ ሆኖ ነው የዘለቀው፡፡ በሁሉም ዘንድ የሚወደድ፣ ሁሉም ሰው ሊጽፍበት የሚፈልግ፤ ሃሳቦቹን የሚያንጸባርቅበት፣ ጽሁፎቹን የሚልክበት ጋዜጣ ነው የሆነው፡፡ አዲስ አድማስ ውስጥ ባሉ አዘጋጆችና ተባባሪ አዘጋጆች ብቻ ሳይሆን ከውጭ እንደ ጋሽ ስብሐት ገብረእግዚአብሔር፣ ኤፍሬም እንዳለ፣ መስፍን ሃብተማርያም ወዘተ ያሉ በርካታ ዕውቅ የብዕር ሰዎች ይጽፉበት ነበር። እነ አብርሃም ረታ ዓለሙን የመሳሰሉ ጸሃፍት ሁሉ የሚጽፉበት ነበር፡፡ አገሪቱ ውስጥ አሉ የተባሉ ጸሃፍት በሙሉ የሚጽፉበት ትልቅ ጋዜጣ ለመሆን የበቃ ነው፡፡
ገጣሚ ነቢይ መኮንን በዋና አዘጋጅነት በጋዜጣዋ ላይ በሰራባቸው ዓመታት የነበረውን ሚና እንዴት ትገልጸዋለህ?
አየህ፣ አሰፋ አርቆ አሳቢ ነበር። አርቆ አሳቢ በመሆኑ ምክንያት አዲስ አድማስ ጋዜጣን ሲጀምር፣ እንደገና “አድማስ ፕሮዳክሽን” በሚል -- ወደ ቴሌቪዥን የማደግ ፍላጎት ነበረው---- እሱን ለማቋቋም ሲሰራ፣ ሙሉ በሙሉ በሚባል ደረጃ የጋዜጣውን ሃላፊነት ለነቢይ ሰጥቶት ነበር። ነቢይ ደግሞ ከአድማስ በፊት በሜጋ ኪነ ጥበባት መጽሔት ያዘጋጅ ስለነበር፣ መልክ ያለው ጋዜጣ እንዲሆን አድርጎታል። ነቢይ ጥሩ ኤዲተር ነው። የቋንቋ ችሎታው በጣም አስደማሚ ነው። ሃሳብን የማዋዛት አቅሙ የላቀ ነው፡፡ በተረት እያዋዛ የሚጽፋቸው ርዕሰ አንቀጾቹ ጎልተው ወጡ እንጂ የግጥም ጥጎቹ ራሳቸው የሚገርሙ ነበሩ። በየሳምንቱ “የግጥም ጥግ” በሚል ግጥሞች የሚያወጣበት ጥግ ነበረው፡፡ ነቢይ አትኩሮ ይሰራ በነበረባቸው ዘመናት ሁሉ ጋዜጣው መልክ ኖሮት እንዲቀጥል የሚችለውን ያህል ጥረት አድርጓል።

የኢሮብ ሕዝብ በኤርትራ ጦር በደል እየደረሰበት መሆኑን የገለፀው የኢትዮጵያ ሕዝባዊ አብዮታዊ ፓርቲ (ኢሕአፓ)፤ የፌደራል መንግስት ይህንን በደል ለማስቆም ምንም ያደረገው ነገር የለም ሲል ተችቷል።
“የትግራይ ሕዝብ አሳር ሊያበቃ ይገባል” በሚል ርዕስ የኢሕአፓ የትግራይ ክልል ቅርንጫፍ ጽሕፈት ቤት ባለፈው ረቡዕ ጥር 14 ቀን 2017 ዓ.ም ባወጣው መግለጫ፣ አንዳንድ የትግራይ ክልል ወረዳዎች ከነሐሴ 28 ቀን 2016 ዓ.ም ጀምሮ በኤርትራ ጦር መያዛቸውን አመልክቷል። በተለይም “ከፍተኛ በደል እያስተናገደ ነው” ሲል ፓርቲው የጠቀሰውን የኢሮብ ሕዝብ ለመታደግ የፌደራል መንግስት “ምንም ዓይነት መፍትሔ” ሲሰጥ አለመታየቱን ጠቅሷል።
አያይዞም፣ የኤርትራ ጦር የኢሮብ ወጣቶችን በገፍ እያፈሰ ወደ ሳዋ ወታደራዊ ማሰልጠኛ ተቋም እየወሰዳቸው እንደሚገኝ የጠቆመው ኢሕአፓ፤ “የትምሕርት ስርዓቱን በመቀየር በኤርትራ የትምሕርት ስርዓት እያስተማረ ይገኛል” ሲል በመግለጫው አትቷል። “ከፍተኛ የአገር ሉዓላዊነት ወረራ” መሆኑን የጠቆመው ፓርቲው፤ የፌደራል መንግስቱ ድርጊቱን የማስቆም ሃላፊነት እንዳለበት አሳስቧል።
በሌላ በኩል፣ በህዝባዊ ወያነ ሓርነት ትግራይ (ህወሓት) አመራሮች መካከል የተፈጠረው መከፋፈልና መወነጃጀል የትግራይ ሕዝብ ሰላምና መረጋጋትን እንዳያገኝ ማድረጉን ፓርቲው አስታውቋል። “እነዚህ በሕዝብ ስም እየማሉ ሕዝብን ለመከራ በዳረጉ ሁለት ሃይሎች የመከኑ ፍላጎቶች የተነሳ የትግራይ ሕዝብ ሁሌም ከጎረቤቶቹ ጋር ጦርነት እየተማዘዘ ሰላም ርቆት ሊኖር አይገባም” ብሏል።
“ሕጋዊ እና ፍትሐዊ” ምርጫ ተካሂዶ የትግራይ ሕዝብ በእንደራሴዎቹ እስኪወከል ድረስ ሁሉንም ሕጋዊ ፓርቲዎች ያካተተ የመማክርት ምክር ቤት እንዲቋቋምም ኢህአፓ ጠይቋል። በህወሓት አመራሮች መካከል በተፈጠረው ውዝግብ የተነሳ የተፈጠሩት ሁለት አንጃዎች “በንግግርና በመቻቻል” አስቸኳይ ሰላማዊና ፖለቲካዊ መፍትሔ ማበጀት እንዳለባቸውም ፓርቲው አሳስቧል።
“በኢትዮጵያ ያሉ ብዙዎቹ የፖለቲካ ፓርቲዎች የትግራይ ሕዝብን የረሱት በሚመስል ሁናቴ አንድም ቀን ስለሕዝቡ ሲጨነቁ አይታይም” በማለት የነቀፋው ኢሕአፓ፤ አገራዊ ፓርቲዎች “ስለትግራይ ሕዝብነ ሲሉ ፖለቲካዊ መፍትሔ ማበጀት” ላይ እንዲሳተፉ ጥሪ አቅርቧል።

 

አንዳንድ ወታደራዊ አመራሮች ውሳኔውን አልተቀበሉትም

የትግራይ ክልል ጊዜያዊ አስተዳደር እንደገና እንዲዋቀር ውሳኔ ማሳለፋቸውን የክልሉ ወታደራዊ አመራሮች አስታውቀዋል። አመራሮቹ ጊዜያዊ አስተዳደሩን አምርረው በመተቸት፣ የአስተዳደሩን አመራሮች “የውጭ ሃይሎች መሳሪያ ሆነዋል“ ሲሉ ከስሰዋል።
ከትላንት በስቲያ ሐሙስ ጥር 15 ቀን 2017 ዓ.ም. ወታደራዊ አመራሮቹ በትግራይ ክልል ለሚገኙ መገናኛ ብዙኃን በሰጡት ጋዜጣዊ መግለጫ፣ ጊዜያዊ አስተዳደሩ የስልጣን ዘመኑን ለማራዘም እየሞከረ መሆኑን ገልጸዋል። “በትግራይ ሃይሎች ላይ የሚካሄደውን የስም ማጥፋት ዘመቻ መከላከል አልቻለም” ሲሉም ተችተዋል፡፡
በአሁኑ ጊዜ በትግራይ ውስጥ ይስተዋላል ላሉት አጠቃላይ ችግር ፖለቲካዊ መፍትሄ እንደሚያሻ የጠቀሱት እነዚሁ አመራሮች፤ “ማንኛውም ነገር ከትግራይ ሃይሎች አቅም በላይ አይደለም።” ሲሉ በመግለጫቸው ተናግረዋል፡፡ “ይህንን ሰበብ በመጠቀም የሚደረግ ጣልቃ ገብነትን አንቀበልም” ሲሉም አክለዋል፡፡
በዶ/ር ደብረጽዮን ገ/ሚካኤል የሚመራው ህወሓት በጊዜያዊ አስተዳደር ያለውን ከ50 በመቶ የዘለለ (50+1) ድርሻውን እንዲረከብ ፍላጎት እንዳላቸው የገለጹት አመራሮቹ፤ “በትግራይ ክልል የሚገኙ ታጣቂዎች በትግራይ ሰላምና ጸጥታ ሴክሬታሪያት ስር መሆን አለባቸው። ከዚህ ውጪ በሆነ ወገን ላይ ግን እርምጃ ይወሰዳል” ሲሉ አስጠንቅቀዋል፡፡
ባለፈው ነሐሴ ወር 2017 ዓ.ም. በዶ/ር ደብረጽዮን ገ/ሚካኤል በሚመራው ህወሓት ለተካሄደው 14ኛ ጠቅላላ ድርጅታዊ ጉባዔ ዕውቅና መስጠታቸውንም ወታደራዊ አመራሮቹ አስታውቀዋል፡፡ አክለውም፤ በጉባኤው ውሳኔ መሰረት፣ የጊዜያዊ አስተዳደር የአመራሮች ለውጥ እንዲደረግ ጥሪ አቅርበዋል።
“በጊዜያዊ አስተዳደሩ ውስጥ ወሳኝ ስልጣን ያላቸው አመራሮችና አባላት ከተሰጣቸው ተልዕኮ ውጪ የሕዝብን ጥቅም ወደ ጎን በመተው ክህደት ፈጽመዋል። የውጭ ሃይል መሳሪያ ሆነዋል” ያሉት ወታደራዊ አመራሮቹ፤ “በፕሪቶሪያ ስምምነት መሰረት የተቋቋመው የትግራይ ጊዜያዊ አስተዳደር ሃላፊነቱን በአግባቡ አልተወጣም” የሚል  ክስ አቅርበዋል። በዚህም ሳቢያ፣ “የተዳከመ ነው” ሲሉ የሰየሙት፣ በአቶ ጌታቸው ረዳ የሚመራው የክልሉ ጊዜያዊ አስተዳደር ተነስቶ በምትኩ ሌላ አስተዳደር እንዲዋቀር መወሰናቸውን አስታውቀዋል፡፡
ይሁንና የወታደራዊ አመራሮቹ ጋዜጣዊ መግለጫ “አይወክለንም” ያሉ ሌሎች ወታደራዊ አመራሮች ደግሞ፣ ጊዜያዊ አስተዳደሩን ኮንነው መግለጫ ያወጡትን ወታደራዊ አመራሮች “አደገኛ አቋም ነው” በማለት ነቅፈውታል። ይህ መግለጫ በህወሓት አመራሮች መካከል የተፈጠረውን ፍጭት ከማባባስ ውጭ የሚበጀው ነገር እንደሌለ ያመለከቱት በሃሳብ “ተለይተናል” ያሉት ወታደራዊ አመራሮች፤ “ከዚህ ከፋፋይ የፖለቲካ ጨዋታ ራሳችንን በማራቅ፣ ከታሪክና ከትውልድ ተጠያቂነት ዕዳ እንድንላቀቅ ጥሪያችንን እናቀርባለን” ብለዋል።
የትግራይ ክልል ጊዜያዊ አስተዳደር በበኩሉ፤ “ከተልዕኳቸው ውጭ ለአንድ ሕገ ወጥ ቡድን ወግነው ጊዜያዊ አስተዳደሩን የማፍረስ፣ ስርዓት አልባነት የማንገስና ሰራዊቱን የመበተን ግልጽ እንቅስቃሴ እያደረጉ መሆናቸውን አሳውቀዋል” በማለት የወታደራዊ አዛዦቹን መግለጫ ወቅሷል። “ሕጋዊም ይሁን ሞራላዊ ቅቡልነት የሌለው” ሲል መግለጫውን ያጣጣለው ጊዜያዊ አስተዳደሩ፤ “የፕሪቶሪያ ስምምነትንም ለአደጋ የሚያጋልጥና ሃላፊነት የጎደለው ነው” ብሏል፣ ከትላንት በስቲያ ሐሙስ አመሻሽ ላይ በይፋዊ የማሕበራዊ ትስስር ገጹ ባወጣው ማብራሪያ።
የክልሉን ጊዜያዊ አስተዳደር የሚነቅፍ መግለጫ ያወጡት ወታደራዊ አመራሮች ከጥር 10 ቀን 2017 ዓ.ም. ጀምሮ ስብሰባ ሲያደርጉ የቆዩ ሲሆን፤ በስብሰባው ላይ ሲሳተፉ የነበሩ አመራሮች ብዛት ወደ 200 ገደማ እንደሚጠጋ ለማወቅ ተችሏል። በአንጻሩ፣ ይህንን የወታደራዊ አመራሮች ጋዜጣዊ መግለጫ የነቀፉና ተጻራሪ መግለጫ ያወጡ ወታደራዊ አዛዦች ብዛት ከ12 በላይ እንደሚሆን ተነግሯል።

በቀጣይ ዓመት ራስ ገዝ ዩኒቨርሲቲ ለመሆን በዝግጅት ላይ ነው

 

ጎንደር ዩኒቨርሲቲ የተመሰረተበትን 70ኛ ዓመትና የማስተማሪያ አጠቃላይ ሆስፒታሉን የመቶኛ ዓመት ምስረታ በዓል በተለያዩ መርሃ ግብሮች ማክበር ጀምሯል። ባለፈው ረቡዕ ጥር 14 ቀን 2017 ዓ.ም የትምህርት ሚኒስቴር ሚኒስትር ብርሃኑ ነጋ (ፕሮፌሰር) በተገኙበት በይፋ የተከፈተው ክብረ በዓል፤ እስከ ሰኔ 30 ቀን 2017 ዓ.ም በተለያዩ ዝግጅቶች እንደሚከበር የዩኒቨርሲቲው ፕሬዚዳንት አስራት አፀደወይን (ዶ/ር) በመክፈቻ ንግግራቸው ገልጸዋል።
በ1942 ዓ.ም ኢትዮጵያ የጤና ሰራተኞች እንደሚያስፈልጋትና የጤና አጠባበቅ ትምህርት የሚቀስሙበት ማሰልጠኛ ተቋም እንዲከፈት የዓለም የጤና ድርጅት ማሳሰቡን ተከትሎ ነው የጎንደር ጤና ማሰልጠኛ ጣቢያ የተቋቋመው፡፡ በወቅቱ ኢትዮጵያዊያን የጤና ባለሙያዎች ስላልነበሩ ወጣቶች እየተመረጡ ውጪ ሐገር እንዲሰለጥኑና የጤና አጠባበቅ ሰራተኞች በሃገር ውስጥ የሚሰለጥኑበት ተቋም እንዲመሰረት የተወሰነ ሲሆን፤ መስከረም 24 ቀን በ1947 ዓ.ም የጎንደር ጤና አጠባበቅ ኮሌጅ ከሐሳብ ወደተግባር መቀየሩን የዩኒቨርሲቲው ታሪክ ይጠቁማል፡፡
ምስረታው እውን እንዲሆን የኢትዮጵያ መንግሥት፣ የዓለም የጤና ድርጅትና የአሜሪካ ዓለም አቀፍ የተራድኦ ድርጅት የተባበሩ ሲሆን፤ በወቅቱ “የጎንደር ጤና ማሰልጠኛ ጣቢያ” በሚል ስያሜ መቋቋሙ ተገልጿል። በዚሁ የምስረታው ዓመት በአገር ግዛት ሚኒስቴር ስር አንድ ዘርፍ ይዞ የነበረው የህዝብ ጤና ጥበቃ ሚኒስቴር በመባል ከፍ ባለ ደረጃ እንዲመራ በነጋሪት ጋዜጣ አዋጅ ቁጥር 91 መታወጁን የሚያትተው የዩኒቨርሲቲው ታሪክ፤ በ1948 ዓ.ም ደግሞ በሐገሪቱ የሚካሄደው ማንኛውም የጤና ትምህርት በሕዝብ ጤና ጥበቃ ሚኒስቴር ስር እንዲተዳደር በመታዘዙ፣ ይህ የማሰልጠኛ ተቋምም በሚኒስቴሩ አመራር ስር እንዲውል መደረጉ ተመልክቷል። ማሰልጠን ከመጀመሩ በፊትም፣ የጤና ማሰልጠኛ ጣቢያ የሚል ስያሜውን በ1947 ዓ.ም ስራውን ሲጀምር፣ የጎንደር ህዝብ ጤና ጥበቃ ኮሌጅና ማሰልጠኛ ወደሚል ቀየረ። ከዚህ በኋላ ብዙ ሂደቶችን ያለፈው ኮሌጁ፤ ከጤና ዘርፍ ውጪ በርካታ የትምህርት ዘርፎችን አካትቶ፣ በ1996 ዓ.ም ጎንደር ዩኒቨርሲቲ ወደሚል ስያሜ መሸጋገሩን ፕሬዚዳንቱ አስራት አፀደወይን (ዶ/ር) አብራርተዋል።
ዩኒቨርሲቲው የተመሠረተበትን 70ኛ ዓመት እያከበረ ባለበት በዚህ ወቅት 11 ኮሌጆች ፣ 87 ቅድመ ምረቃ እና 280 ድህረ ምረቃ፣12 የምርምር ማዕከላት፣ ከተለያዩ ወረዳዎች እስከ መዲናዋ አዲስ አበባ ድረስ 22 የምርምርና የስልጠና እንዲሁም የማህበረሰብ አገልግሎት መስጫ ግቢዎች ያሉት አንጋፋና ግዙፍ የትምህርት ልህቀት ማዕከል መሆኑ ተነግሯል፡፡ በአሁኑ ወቅት ዩኒቨርሲቲው ከ40 ሺህ በላይ ተማሪዎችን በማስተማር ላይ የሚገኝ አንጋፋ የልህቀት ማዕከል መሆኑም ተጠቁሟል፡፡
ዩኒቨርሲቲው የመጀመሪያዎቹን ተማሪዎች በ1958 ዓ.ም ያስመረቀ ሲሆን፤ ከዚህ ጊዜ ጀምሮ እስከ 2016 ዓ.ም ድረስ በተለያዩ ዘርፎች ከ100 ሺህ በላይ ተማሪዎችን በማስመረቅ ለሃገሪቱ የሰለጠነ የሰው ሃይል በማበርከትም ሚናው የጎላ እንደሆነ ፕሬዚዳንቱ ገልፀዋል።
ዩኒቨርሲቲው ለሃገራቸው ከፍተኛ አስተዋፅኦ ላበረከቱ 10 ሰዎች የክብር ዶክትሬት የሰጠ ሲሆን፤ በቀጣይ ዓመት ከአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ቀጥሎ ራስ ገዝ ዩኒቨርስቲ ለመሆን በዝግጅት ላይ እንደሚገኝና በአገር ውስጥና ከአገር ውጪ የሚገኙ ከ150 በላይ አጋር ተቋማት እንዳሉት ለማወቅ ተችሏል።
ከጣሊያን ወረራ ጊዜ ጀምሮ ታሪክ ያለው የዩኒቨርስቲው አጠቃላይ የማስተማሪያ ሆስፒታል፤ ለጎንደርና ለአካባቢው ህዝብ ጤና ታሪክ የማይዘነጋው ውለታ መዋሉ የተገለፀ ሲሆን፤ 100ኛ ዓመቱን መድፈኑ ታሪኩን ያጎላዋል ተብሏል። በጎንደር ከተማ እስከ ቅርብ ጊዜ ድረስ ብቸኛው ሆስፒታል በመሆን በማከም፣ በምርምር፣ በግንዛቤ ማስጨበጥና በማስተማሪያነት ያገለገለው ይሄው ሆስፒታል፤ አሁንም ከአማራ ክልል የተለያዩ አካባቢ ዎች ለሚመጡ ከቤኒሻንጉልና ከሱዳን ጭምር ለሚመጡ በአጠቃላይ ለ13 ሚሊዮን ህዝብ ሪፈራል ሆኖ እያገለገለም ነው ተብሏል።
ጎንደር ዩኒቨርሲቲ በትምህርት ልህቀትና በጤና አገልግሎት የደረሰበትን የ70 እና የመቶ ዓመት ስኬት፤ ከጥር 14 እስከ ሰኔ 30 ቀን 2017 ዓ.ም ድረስ በተለያዩ መርሃ ግብሮች እያከበረ እንደሚቆይ የተገለጸ ሲሆን፤ ከመርሃ ግብሮቹም መካከል ሩጫን ጨምሮ ስፖርታዊ ውድድሮች፣ ነፃ የጤና ምርመራ፣ ደም ልገሳና ሌሎች የማህበረሰብ አገልግሎቶች ይገኙበታል፡፡ የጎንደር ቃልኪዳን ቤተሰብ ቀን፣ የህክምና ተማሪዎች ምረቃ በዓል፣ የታዋቂ ሰዎች ስኬትና ተሞክሮ ማካፈያ መድረክ፣ የፕሮጀክት ስራዎች ምርቃት፤ የአውደ ርዕይ መርሃ ግብር፣ የጥናትና ምርምር ጉባኤና ሌሎችም የመርሃ ግብሩ አካል እንደሚሆኑ ለማወቅ ተችሏል፡፡
የበዓል አከባበሩ ከዩኒቨርሲቲው 60ኛ ዓመት አከባበር ልምድና ከውጪ አገር ተሞክሮ ተቀምሮ ትላንትን፣ ዛሬንና ነገን የሚያስተሳሰር ታሪካዊ አከባበር እንዲሆን ታስቦ ከፍተኛ ዝግጅት እንደተደረገበት ፕሬዚዳንቱ አስራት አፀደወይን (ዶ/ር) አብራርተዋል።

 

 

የውጭ ምንዛሪ ለማግኘት ባንኮች የሚጠይቁት የማስያዣ ብር መጠን ከፍተኛ መሆኑ እንቅፋት ፈጥሯል ተብሏል። የኢንዱስትሪ ሚኒስቴር ሚኒስትር አቶ መላኩ አለበል እንደተናገሩት፣ ባንኮች ለአምራች ዘርፍ ሲያቀርቡት የነበረው ከ13 በመቶ የማይበልጥ የብድር አቅርቦት ድርሻ ወደ 24 በመቶ እንዲያድግ የፖሊሲ አቅጣጫ ቢሰጥም፣ የብድሩ ድርሻ ግን እስካሁን ከ16 በመቶ አልበለጠም።
ከትላንት በስቲያ ጥር 15 ቀን 2017 ዓ.ም. የሚኒስቴር መስሪያ ቤታቸውን የስራ አፈጻጸም ሪፖርት ለሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ያቀረቡት አቶ መላኩ፤ ለከፍተኛ አምራች ኢንዱስትሪዎች 28 ነጥብ 7 ቢሊዮን ብር በብድር መልኩ ለማቅረብ ታቅዶ የነበረ ሲሆን፣ ከዕቅዱ የተሳካው 24 ነጥብ 87 ቢሊዮን ብር መሆኑን አብራርተዋል። ይህ ብድር ከዕቅዱ አንጻር ዝቅ ያለ ቢሆንም፣ ከዓምናው ተመሳሳይ ወቅት ጋር ሲነጻጸር ግን 4 ነጥብ 9 በመቶ ብልጫ ማሳየቱን ጠቁመዋል፡፡
ባንኮች ለአነስተኛና መካከለኛ አምራች ኢንዱስትሪዎች ስራ ማስኬጃ የሚሰጡት ብድር ካላቸው ካፒታል ከ1 በመቶ ያልበለጠ እንደነበር ያነሱት ሚኒስትሩ፤ በአሁኑ ወቅት ግን ድርሻው ወደ 10 ነጥብ 3 በመቶ ከፍ እንዲል መደረጉን ገልጸዋል።
“የኢትዮጵያ ባንኮች ለአምራች ኢንዱስትሪው ፋይናንስ ከማቅረብ ይልቅ በተለመደው መንገድ የአጭር ጊዜ ትርፍ በሚያስገኙና ስጋታቸው ዝቅተኛ በሆኑ ዘርፎች ላይ እንደተሰማሩ እንዳይቀጥሉ ማድረግ የሚቻልበትን አሰራር መፈተሽ ይገባናል” ያሉት ሚኒስትሩ፤ በዚህ ረገድ መንግሥት በቀጣይ ሊወስድ የሚችለውን እርምጃ ጠቁመዋል።
ባለፉት ስድስት ወራት ለአምራች ዘርፉ የግብዓት አገልግሎት ለማቅረብ ታቅዶ ከነበረው 468 ሚሊዮን ዶላር ማቅረብ የተቻለው 369 ሚሊዮን ዶላር ገደማ መሆኑን በመግለጽም፣ባንኮች የሚጠይቁት ማስያዣ ብር መጨመሩ ለዕቅዱ አለመሳካት ምክንያት እንደሆነም ጠቅሰዋል፡፡
 ባንኮች ለአምራች ዘርፍ ሲያቀርቡት የነበረው ከ13 በመቶ የማይበልጥ የብድር አቅርቦት ድርሻ ወደ 24 በመቶ እንዲያድግ የፖሊሲ አቅጣጫ ቢሰጥም፣ የብድሩ ድርሻ ግን እስካሁን ከ16 በመቶ አለመብለጡን ሚኒስትሩ ተናግረዋል።
የውጭ ምንዛሪ ለማግኘት ባንኮች የሚጠይቁት የማስያዣ ብር መጠን “ከወትሮው ከፍ ያለ” በመሆኑ ምክንያት በታቀደው ልክ ስኬታማ ለመሆን እንቅፋት መፍጠሩን አቶ መላኩ ገልጸዋል፡፡ “ከተሟላ የማክሮ ኢኮኖሚ ማሻሻያ ጋር በተያያዘ የብር ፍላጎት መጠን በእጥፍ ስለጨመረ፣ አቅርቦቱ ‘አጥጋቢ ነው’ ተብሎ ሊወሰድ የሚችል አይደለም” ሲሉ ለሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት በሰጡት ማብራሪያ አስረድተዋል። ዘርፉ የሚፈልገውን በቂና ውጤታማ ፋይናንስ ለማቅረብ ባንክ እና ባንክ ነክ ያልሆኑ ሌሎች የፋይናንስ ምንጮችን መጠቀም አስፈላጊ መሆኑንም ጠቁመዋል።

ሁለት ዕውቅ ሽማግሌዎች ወዳጃቸው ለሆነ አንድ ሽማግሌ፤ “ሴት ልጅህን ለልጄ ስጠኝ” እያሉ በተራ በተራ መልዕክተኛ ላኩበት። ያም ሽማግሌ መልክተኞቹን በተራ በተራ አስተናገዳቸው። ለመጀመሪያው መልዕክተኛ፡- “መልካም፤ ልጄን ለልጅህ እሰጥሃለሁ ግን ቤትህን አሰናዳ ብለህ ንገረው” ብሎ ይልክበታል።
ለሁለተኛው መልዕክተኛም፤ “ና ቅረብ ወዳጄ። ለጌታህ ስትለው፤ ደግ ነው ልጄን ለልጅህ ልድራት ዝግጁ ነኝ፤ ሆኖም አስቀድመህ ቤትህን አሰናዳ” አለው። መልዕክተኞቹም-እርስ በእርሳቸው የተባሉትን ሳይነጋገሩ ወደ ጌቶቻቸው ሄዱ።
አንደኛው መልዕክተኛ ወደ ጌታው ሄዶ፤ “ጌታዬ ጥያቄውን አቅርቤ ነበር። ነገር ግን የ3 ወር ጊዜ ሰጥቼሃለው፤ ቤትህን አሰናዳ በለው” አሉ።
በመጀመሪያ መልሱን የሰማው ሽማግሌ ለልጁ፤ “በል ወዳጄ ሦስት ወር ቅርብ ጊዜ ነው፤ በያለበት መሬት እየገዛህ እልፍኝና አዳራሽ ሥራ፡፡ ለሚስትህና ላንተ መቀመጫ ይደላሃል” አለው፡፡
በሁለተኛ ደረጃ መልሱን የሰማው ሽማግሌ ግን፤ “ያጅሬን ብልሃት እኔ አውቃለሁ። በል ልጄ ተነስተህ ገንዘብ ይዘህ ሄደህ ወዳጅ አብዛ። እስካሁን የምታውቀው ሰው በቂ አይደለም። ቤትህን አሰናዳ ማለቱ ትርጉሙ ይሄ ነው።”
የተባለው ቀን ሲደርስ አባት ደግሶ ይጠባበቅ ኖሯል። ሁለቱ አባቶች በሰዓቱ ከች አሉ። ከተጋበዙ በኋላም አንደኛው፤ “መሬት ገዝቼ ለልጄ ሰጥቼዋለሁ።” ሲል ተናገረ።
የሠርጉ ባለቤትም፤ “የምድር ብዛት ከቁም-ነገር አይውልም። ባንድ ስተት ቀሪ ነው። እልፍኝና አዳራሹንም አውሎ ነፋስ ይጠርገዋል። የእሳት እራትና ምሳ ነው። ውሃ ሙላት ያጠፋዋል። ጠንቅ አያጣም” አለው።
ቀጥሎም ሁለተኛው አባት፤ “ገንዘብ ይዘህ ሂድ፤ ወዳጅ አብዛ” ብዬዋለሁ አለና አስረዳ። የሠርገኛው አባትም፤ “ሌላ ሀብት ሁሉ ጠፊ ረጋፊ ነው። ብዙ ወዳጅ ግን በየቦታው ቢፈራ ሀብት ነው። ጥቅምም ካንዱ ቢጠፋ ካንዱ ይገኛል፤ አንዲት ልጄን ለዚህ ልጅ መርቄ ሰጥቼዋለሁ” አለ።
* * *
ህዘብ የሚወደው መሪ ማግኘት ታላቅ ጸጋ ነው። ወዳጅ ለማፍራት የሚችል መሪ ማግኘት መታደል ነው። ለራሱ ማረፊያ እልፍኝ - ከአዳራሽ የሚሰራ መሪ ማግኘት ከቁምነገር የሚጻፍ አይደለም። ባንድ ስተት ቀሪ-ነው፤ አውሎ ንፋስ ይጠርገዋል። ህዝብ የክብሩ ምልክት የሚሆንለት መሪ ይፈልጋል። ተናግሮ የሚያጠግበው መሪ ይፈልጋል። እምነቱን የሚጥልበት፣ ለሾመው የሥልጣን ዘመን የሚበቃ ጥንካሬ ያለው ርዕሰ-ብሔር እንዲኖረው ይመኛል። በእርግጥም ህዝብ ሆደ-ሰፊ፣ እንደ ወጣት የማይቸኩል፣ በረዥምና በበሳል አካሄድ እንጂ በቆረጣ የማይመካ፣ ብልጥ ሳይሆን ብልህ የሆነ፣ የዕውቀት-የልምድና የዕድሜ ባለፀጋ የሆነ እንደራሴ ይፈልጋል።
የሀገር መሪ ሲመረጥ እንደ ቴአትር ገፀ-ባህሪ ለአንድ ወንበር (ሚና) ሁለት ሰው የሚሰለጥንበት (Double-cast እንደሚባለው) የመጠባበቂያ ሂደትም ሆነ መለዋወጫ የለውምና፣ አካላዊና አዕምሮአዊ ይዞታውና ብቃቱ በቅጡ መጤን ይኖርበታል።
የሕዝብ ስነ-ልቦናን የሚያሸንፍ መሪ የህዝብን ተስፋ ያለመልማል። መሪው ተስፋ የማይጣልበት ከሆነ፣ ተመሪውንም ይዞት ወደ ጨለምተኛ አቅጣጫ ያመራል። ዣን ፖል ሮችተር እንዳለው፤ “የእርጅና አሳዛኙ ነገር፤ ደስታችን ማለቁ ሳይሆን፤ ተስፋችን ጨርሶ መሟጠጡ ነው”። ተስፋ ያለው መሪ፤ የሆነ እንደሆነ ለነገ መቅረዝ ያበራል። ልምዱን፣ እውቀቱን፣ ደርዙን እንደ ሻማ እያቀጣጠለ የመጪውን ቀን ተስፋ የማያሳይ መሪ፣ አለቃ ወይም ሹም ከሆነ ግን ጭል-ጭል ትል የነበረችውን ነግ- ተነግ- ወዲያ ራዕይ ይጋርዳል። እርጅና ፀፀት የሚያመጣው ያልተዘጋጁበትን ቦታ እንደማታ-ሲሳይ፣ እንደማታ-እንጀራ ቆጥረው ሲቀመጡ ነው። “ምነው እዚህ እንደምደርስ ባወቅሁ፣ ራሴን በተሻለ ጠብቄ እቆይ ነበር” እንዲል ኡቢ ብሌክ፤ በስተርጅና የሚገኝ ሥልጣን ከትፍስህቱ ጭንቀቱ፣ ከተስፋው ፀፀቱ ይብሳል፡፡ እንደ ኖስትራ ዳሙስ The man who saw tomorrow ማለታችን ይቀርና The Man who’ll see Yesterday የሚል ዓይነት፤ ምስቅልቅል ውስጥ ሊከተንም ይችላል። (ራዕያችን ነገን አስቀድሞ ማየት መሆኑ ይቀርና፤ ትላንትን ነገ ለማየት መቋመጥ ይሆናል እንደማለት ነው።)
“የአንበሳ መንጋ መሪ በግ ከሚሆን ይልቅ፣ የበግ መንጋ መሪ አንበሳ ቢሆን ይሻላል” ሲል የፃፈልን ዳንኤል ዴፎ፤ የአገርን ምልክት፣ የአገርን መኩሪያ፣ የአገርን ወኪል፣ የኢገርን እንደራሴ ጉልህ ገጽታ አበክሮ ሲገልጽልን ነው። አንድም “ምነው ወጣቱ ባወቀ፣ ምነው ሽማግሌው መሥራት በቻለ” የሚለው የፈረንሳዮች አባባል፣ የዕውቀትንና የሥራን ኅብራዊ አስፈላጊነት ሲያሳየን ነው።
የነፃነትን፣ የፍትሕን፣ የመብት መከበርን ፍቱን አስፈላጊነት ከመቼውም በበለጠ እያየች፣ በላቀ ሁኔታም እየተገነዘበች፣ በመጣችው ሀገራችን ውስጥ ለዚህ እውን መሆን ብርቱ ጥረት የሚያደርጉ ብቁ ዜጎችን እንሻለን። ፈረንጆቹ እንደሚሉት፤ The Young man knows the rules the old man knows the exceptions (ወጣቱ በህግ የሚፈቀደውን ያውቃል፤ ሽማግሌው በሕግ የሚከለከለውን ያውቃል) ብለን እንዳናልፍ የሀገር ክብር፣ የመንበሩ ልዕልናና የታሪክ አደራ እንቅልፍ ይነሱናል።
ለአንድ የኃላፊነት ቦታ የብቃት መመዘኛ የዚህ ወይም የዚያ ብሔር-ብሔረሰብ መሆኑ እንዳይደለ መቼም ከመቼውም ጊዜ ይልቅ ዛሬ ሳንረዳው አይቀርም፡፡ በተግባር መከወኑ ላይ ባይሳካልንም፡፡
የአእምሮ መትባት፣ የአንጎል ብስለት፣ የእውቀት ደረጃና የሙያ ክህሎትና ሥነ-ምግባር እጅግ ወሳኝ የመሆኑን ያህል፤ የእነዚህ ሁሉ ማቀፊያ የሆነው አካላዊ ውሃ-ልክና ጤነኛነት፣ እንዲሁም የእድሜ ልከኛነት የዚያኑ ያህል ወሳኝ ነው። ይህ ባልተሟላበት ሁኔታ ኃላፊነትና ሥልጣን አካላዊ ሸክም ሲሆን፤ ውሎ አድሮም አዕምሮአዊ ጭንቀት ወደመሆን እንዳይሄድ መስጋት ተገቢ ነው። “አይቶ ነው ገምቶ ነው…” እንዲሉ ዕድሜንም አቅምንም አገናዝቦ ኃላፊነትን መቀበል ደግ ነው። አለበለዚያ እድሜ እየገፋ ሲሄድ፤ ህዝብንም “ማንስ ቢወክልህ ምን ቸገረህ?” ብሎ እንደመናቅ ያለ ክፉ ደዌ የለም። ሌላ “ጥገኛ ዝቅጠት” መጋበዝም ይሆናል ዞሮ ዞሮ። ደግሞምም የሁሉም ኃላፊነት ነው- የአጪም፣ የታጪም፣ የ”እሰይ-አበጀህ የእኛ ሎጋ!” ባይ ታዳሚም። አለበለዚያ፤
“ሰማንያውን ነህ
ዘጠናውን ነህ
ወገቤን የያዝከኝ ገላጋይ መስለህ!”
ማለት ይመጣል። ኃላፊነቱም አጠያያቂ ይሆናል። ሁሉም ጥንቃቄ ያሻዋል።

 

Saturday, 18 January 2025 22:02

መልካም የጥምቀት በዓል

ከአገራዊ የምክክር ሂደቱ ራሱን ማግለሉን ያስታወቀው የሲዳማ ፌደራሊስት ፓርቲ፤ “አገራዊ የምክክር ሂደቱ መደበኛ ሕዝባዊ ውይይት እየመሰለ ሂዷል” ሲል ተቸ።
ባለፈው ረቡዕ ጥር 7 ቀን 2017 ዓ.ም. ፓርቲው ለኢትዮጵያ አገራዊ ምክክር ኮሚሽን በጻፈው ደብዳቤ ላይ እንደገለፀው፤ “አካታች” እና “ገለልተኛ” ምክክር የሚካሄድበት ዕድል ስለሌለ ራሱን ከምክክር ሂደቱ አግልሏል። አክሎም፣ የምክክር ኮሚሽኑ “ከገዢው ፓርቲ ተጽዕኖ” ውጪ መሆን አለመቻሉን ጠቅሷል።
የምክክር ሂደቱ የሃሳብ ልዩነት ያላቸውንና “የግጭቶቹ ተዋናይ የሆኑትን አካላት ያላሳተፈ”፣ “ጦርነቶች እንዲቆሙ በማድረግ አስቻይ ሁኔታን ያልፈጠረ” መሆኑን ፓርቲው አመልክቷል። ይህም ሁኔታ ከአጀንዳ ልየታ ሂደት ጀምሮ ሲስተዋል መቆየቱን ጠቁሟል።
ምክክሩ “መደበኛ ሕዝባዊ ውይይት እየመሰለ ሄዷል” ያለው ፓርቲው፣ አሁን ኮሚሽኑ እየተከተለ ባለው መንገድ “የተወሳሰቡ” ያላቸው የአገሪቱ ችግሮች እንደማይፈቱ በጽኑ እንደሚያምንም ነው ያስረዳው። ፓርቲው ከኮሚሽኑ ጋር የመግባቢያ ስምምነት ከተፈራረመ ወዲህ፣ በመንግስት አካላት በተለይም የክልሉ መንግስት ከዚያ በፊት ከነበረው “በከፋ ሁኔታ” ዕመቃ እንደተፈጸመበት አብራርቷል።
በዚህ ምክክር መሳተፍ ችግሮችን የሚፈታ ውጤት ያመጣል ብሎ እንደማይጠብቅም ፓርቲው አመልክቷል። የምክክር ሂደቱ አሁን ባለው ቁመና “ከገዢው ፓርቲ ፍላጎት ውጪ ለሌሎች አስቻይ ሁኔታ መፍጠር የማይችል፣ አካታችና ሃቀኛ አገራዊ ምክክር በማድረግ ውስብስብ ችግሮቻችን በምክክር ለመፍታት የሚያስችል አቅምና ቁርጠኝነት የሌለው መሆኑን” እንዳረጋገጠ በደብዳቤው ላይ ጨምሮ አትቷል።
ኮሚሽኑ በነሃሴ ወር 2016 ዓ.ም. ባካሄደው የአጀንዳ ማሰባሰብ ሂደት፣ ከፓርቲው ከታገዱ ግለሰቦች ጋር በመተባበር የፓርቲው ተወካዮች ከመድረኩ ተገድደው እንዲወጡ “አድርጓል” በማለትም ፓርቲው ከስሷል። አያይዞም፣ ፓርቲው “ይህም የተደረገው በዲሲፕሊን ከተሰናበቱ የፓርቲውን ሰዎች ቀድሞውኑ በማስገባትና ከእነርሱ ጋር በማበር ነው” ያለ ሲሆን፣ ቦርዱ ችግሩን ለማስተካከል ከፓርቲው አመራር ጋር ተወያይቶ ከስምምነት ላይ የደረሰ ቢሆንም፣ በተስማማው መሰረት ምንም ዓይነት እርምጃ አለመውሰዱን ነው የጠቀሰው።

የፌደራል መንግስት ለፕሪቶሪያው የሰላም ስምምነት ተገዢ እንዲሆን ተጠይቋል። ለሁለት የተሰነጠቁት የትግራይ ክልል ጊዜያዊ አስተዳደር እና ህዝባዊ ወያነ ሓርነት ትግራይ (ህወሓት) አመራሮች ሃላፊነታቸውን በአግባቡ እንዲወጡም ጥሪ ቀርቧል።
ከባለፈው ሰኞ ጥር 5 ቀን 2017 ዓ.ም ጀምሮ ለተከታታይ ሁለት ቀናት በትግራይ ክልል፣ መቐለ ከተማ፣ ሮማናት አደባባይ የተካሄደው የተቃውሞ ሰልፍ ላይ የተገኙ ተፈናቃዮች ተቃውሟቸውን ማሰማታቸው ተገልጿል። በዚሁ የተቃውሞ ሰልፍ ላይ ከተነሱ ጥያቄዎች መካከል፣ “ይበቃል፣ ወደ ቀድሞ ቀያችን መልሱን!” የሚለው መፈክር በዋናነት ሲስተጋባ እንደነበር ተጠቅሷል።
የተቃውሞ ሰልፉ ከቀን በተጨማሪ በምሽትም ሲካሄድ የቆየ ሲሆን፣ ከተፈናቃዮች ባሻገር በተለያዩ የሞያ ዘርፎች የተሰማሩ የመቐለ ከተማ ነዋሪዎች እንደተሳተፉበት ለማወቅ ተችሏል። በርካታ የከተማዋ ጎዳናዎች ተዘግተው መታየታቸውን እንቅስቃሴውን በቅርበት የተከታተሉ ወገኖች ለአዲስ አድማስ እንደጠቆሙት፣ በርካታ የክልሉ የፖሊስ ሃይል አባላትም በጎዳናዎቹ ላይ ተሰማርተው ነበር።
የትግራይ ክልል ጊዜያዊ አስተዳደር የተቃውሞ ሰልፉ በተጀመረበት ዕለት ባወጣው መግለጫ፣ የተፈናቃዮችን ጥያቄ እንደሚደግፍ አስታውቋል። አስተዳደሩ፣ “’ይበቃል፣ ወደ ቀያችን መልሱን’ በሚል መሪ ቃል በተፈናቃዮች አማካይነት የተጠራው ሰላማዊ የተቃውሞ ሰልፍ ቀናና የሚደገፍ ነው” ብሏል።
“ተፈናቃዮቹ እየደረሰባቸው ላለው መከራ ተገቢ ምላሽ እየተሰጠ አይደለም” በማለት መግለጫውን የቀጠለው ጊዜያዊ አስተዳደሩ፣ “የፌደራል መንግስት የገባውን ውልና ቃል በመተግበር ተፈናቃዮች ወደ ቀያቸው መመለስ አለበት” ሲል አሳስቧል። “አሁንም በፕሪቶሪያ የሰላም ስምምነት መሰረት ከአገር መከላከያ ሰራዊት ውጪ ያሉ ታጣቂ ሃይሎች ከትግራይ ክልል ይውጡ፤ በሕገ መንግስቱ አማካይነት፣ የትግራይ ክልል ግዛታዊ አንድነት ተከብሮ ተፈናቃዮች ወደ ቀያቸው መመለስ አለባቸው” ሲልም በመግለጫው አፅንኦት ሰጥቷል።
ከዚህ በተጓዳኝ፣ የአፍሪካ ሕብረት፣ አሜሪካ፣ የአውሮጳ ሕብረትና የዓለምአቀፉ ማሕበረሰብ የትግራይ ሕዝብን ድምጽ በማዳመጥ የፕሪቶሪያ ውል በአግባቡ ተግባራዊ እንዲሆን ጫናቸው እንዲያሳድሩ ጥሪ አቅርቧል፣ ጊዜያዊ አስተዳደሩ።
“ጽላል ሲቪክ ማሕበር ማሕበረሰብ ምዕራብ ትግራይ” በተሰኘ ድርጅት አስተባባሪነት ሲደረግ የቆየው የተቃውሞ ሰልፍ፣ ባለፈው ረቡዕ ጥር 7 ቀን 2017 ዓ.ም ሲደመደም፣ ተፈናቃዮች በበኩላቸው የአቋም መግለጫ አውጥተዋል። በዚህ የአቋም መግለጫ የፌደራል መንግስት ለፕሪቶሪያ የሰላም ስምምነት ታማኝና ተገዢ በመሆን ስምምነቱን በሙሉነት እንዲያስፈፅም ጥሪ አቅርበዋል።
የዓለም አቀፉ ማሕበረሰብ የፕሪቶሪያ የሰላም ውል እንዲፈረም ያሳየው ቁርጠኝነት ገቢራዊ እንዲሆን ሚናውን ማጉላት እንዳለበት ያነሱት ተፈናቃዮቹ፣ የትግራይ ክልል በሕገ መንግስቱ መሰረት ወደ “ቀድሞ ይዞታው” እስከሚመለስ ድረስ ሰላማዊ ተቃውሞ ማሰማታቸውን እንደሚቀጥሉ በአቋም መግለጫቸው ገልጸዋል። በተጨማሪም፣ የትግራይ ክልል ጊዜያዊ አስተዳደርና የህዝባዊ ወያነ ሓርነት ትግራይ (ህወሓት) ከፍተኛ አመራሮች ለስልጣን ሲሯሯጡ የተፈናቃዮችን ስቃይ “ዘንግተዋል” ሲሉ ምሬታቸውን ያሰሙት እነዚሁ ሰልፈኞች፣ “ያለፈው ይበቃል፣ አሁን የተጣለባችሁን ሃላፊነት በአስቸኳይ ተወጡ!” በማለት ጥሪ አቅርበዋል።
የተቃውሞ ሰልፉ ተሳታፊዎች ለትግራይ ክልል ጊዜያዊ አስተዳደር ፕሬዝዳንት አቶ ጌታቸው ረዳ፣ ለህወሓት ሊቀ መንበር ዶክተር ደብረጽዮን ገብረሚካኤል፣ እንዲሁም ለተባበሩት መንግስታት ድርጅትና፣ በክልሉ ለሚገኙ የዕርዳታ ድርጅቶች የአቋም መግለጫቸውን ማድረሳቸውን ለማወቅ ተችሏል።

 

• በሰላም ስም የሚደረጉ ሸፍጦች ይቁሙ ተባለ

በቤንሻንጉል ጉምዝ ክልል፣ መተከል ዞን፣ ግልገል በለስ ከተማ የሚገኝ አንድ ኬላ ለዜጎች ሞት ምክንያት መሆኑ ተገለፀ። ከግድያ በተጨማሪ፣ በአካባቢው የሚንቀሳቀሱ ታጣቂዎች የዕገታ ተግባር እንደሚፈጽሙ ተነግሯል።
ከግልገል በለስ ከተማ በቅርብ ርቀት በሚገኘውና “ቻይና ካምፕ” ተብሎ በሚጠራው ኬላ ላይ በርካታ ዜጎች በማንነታቸው እየተለዩ መገደላቸውን እናት ፓርቲ ባለፈው ሰኞ ጥር 5 ቀን 2017 ዓ.ም. ባወጣው መግለጫ አስታውቋል። የአካባቢው ነዋሪዎች በተደጋጋሚ “የኬላው መኖር ምክንያታዊ ያልሆነና አላስፈላጊ ነው” የሚል ቅሬታ ሲያቀርቡ ቢቆዩም፣ ሰሚ ሊያገኙ አለመቻላቸውን ፓርቲው በመግለጫው ላይ አመልክቷል።
ኬላው ላይ ተሽከርካሪዎችን በማስቆም ታጣቂዎቹ ተሳፋሪዎችን በማንነት እየለዩ እንደሚሰውሩ፣ እንዲሁም በአሰቃቂ ሁኔታ እንደሚገድሉ ነዋሪዎች መናገራቸውን ፓርቲው የጠቀሰ ሲሆን፣ ነዋሪዎች “በአጠቃላይ የግልገል በለሱ “ቻይና ካምፕ” ኬላ የዜጎች ድብቅ ግድያ ‘ማመቻቻ ነው’ ብሎ መደምደም ይቻላል” ማለታቸውንም አክሎ አትቷል።
ታህሳስ 24 ቀን 2017 ዓ.ም. ከቀኑ ስድስት ሰዓት አካባቢ ወደ ግልገል በለስ ከተማ ይገባ የነበረውን የሕዝብ ማመላለሻ ተሽከርካሪ ቻይና ካምፕ ኬላ ላይ ታጣቂዎቹ አስቁመው ለስራ ይጓዝ የነበረን አንድ ወጣት “የዓይንህ ቀለም አላማረንም” በሚል ምክንያት ከቆመው ተሽከርካሪ አስወርደው “በአሰቃቂ ሁኔታ” መግደላችውን እናት ፓርቲ ገልጿል። የተፈጸመውን ግድያ የተመለከቱ ተሳፋሪዎች በከተማው ውስጥ ለሚገኘው መከላከያ ሰራዊት ስለሁኔታው ቢያስታውቁም፣ “ትዕዛዝ አልተሰጠንም” በሚል እርምጃ ከመውሰድ መታቀባቸውን የጠቆመው ፓርቲው፣ “’ቻይና ካምፕ’ እና ‘ኪዳነምሕረት ሰፈር’ በተባሉ አካባቢዎች ተገቢ ማጣራት ቢደረግ፣ ሌሎች የግድያ መረጃዎች ይገኛሉ። ነገር ግን መሰል ድርጊቶች እንዳይጋለጡ ከፍተኛ ርብርብና ማድበስበስ አለ” በማለት አስረድቷል።
ይህንን የግድያ ድርጊት “ፈጽመዋል” የተባሉት ታጣቂዎች ከዚህ ቀደም ጫካ ውስጥ ሲንቀሳቀሱ እንደ ነበሩና ከክልሉ መንግስት ጋር ዕርቅ ማውረዳቸውን እናት ፓርቲ ጠቅሶ፣ እነዚሁ ታጣቂዎች ከ”ቻይና ካምፕ” ኬላ አካባቢ ወታደራዊ ካምፕ ተሰጥቷቸው ሰፍረው እንደሚገኙ አብራርቷል። በተጨማሪም ፓርቲው “በሰላም ስም ቡድኖችን እየቀለቡ ማንነት ተኮር ጭፍጨፋና እገታ ይፈጽማሉ” በማለት በክልሉ መንግስት አካላት ላይ ነቀፌታውን አሰምቷል።
“በሰላም ስም የሚደረጉ ሸፍጦች ይቁሙ” ሲል ጥሪ ያቀረበው እናት ፓርቲ፣ የድርጊቱ ፈፃሚዎች ለሕግ እንዲቀርቡ ጠይቋል። ፓርቲው አያይዞም፣ የግልገል በለስ ከተማ ነዋሪዎችን “ለከባድ ሰቆቃ እየዳረገ ነው” ሲል የጠቀሰውን ቻይና ካምፕ ኬላ “ሕዝቡን በማወያየት” በአስቸኳይ እንዲነሳ ተማጽኗል።
ተጨማሪ ድብቅ መቃብሮች “አሉባቸው” ተብለው በአካባቢው ነዋሪዎች የሚጠረጠሩ እንደ ”ቻይና ካምፕ” እና “ኪዳነምሕረት ሰፈር” ዓይነት ስፍራዎች በኢትዮጵያ ሰብዓዊ መብቶች ኮሚሽንና መሰል ተቋማት ምርመራ ተደርጎባቸው ውጤቱ ለሕዝብ ይፋ እንዲሆን እናት ፓርቲ አሳስቧል። እንዲሁም “አንዳንድ የመንግስት ባለስልጣናት ያላቸው ሚና የምርመራው አካል እንዲሆን እንጠይቃለን።” ብሏል፣ ፓርቲው በመግለጫው።

 

Page 4 of 753