Administrator

Administrator

 የአርጀንቲና ፓርላማ የአገሪቱ ሴቶች ባረገዙ በሁለት ሳምንታት ጊዜ ውስጥ ጽንስ ማቋረጥ እንዲፈቀድላቸው የሚደነግገውን ረቂቅ ህግ ውድቅ ማድረጉ በበርካታ የአገሪቱ ዜጎች ዘንድ ተቃውሞ ቢገጥመውም፣ድጋፋቸውን የገለጹ እንዳሉም ተዘግቧል፡፡
የፓርላማው አባላት በረቂቅ ህጉ ላይ ለ15 ሰዓታት ያህል ክርክር ካደረጉ በኋላ 38 ለ32 በሆነ አብላጫ ድምጽ ህጉ ውድቅ መደረጉን የዘገበው ዘ ጋርዲያን፤ ይህም የሴቶች መብት ተሟጋች ተቋማትንና በርካታ የአገሪቱ ዜጎችን ማስቆጣቱን ጠቁሟል፡፡
የካቶሊካዊት ቤተ ክርስቲያን፣ የፓርላማ አባላቱ ህጉን እንዳያጸድቁት ግፊት አድርገዋል፣ ሴቶች ጽንስ የማቋረጥ መብታቸው ሊከበርላቸው ይገባል በሚል የመብት ተሟጋቾቹ ተቃውሟቸውን መግለጻቸውን የጠቆመው ዘገባው፤በርካታ ቁጥር ያላቸው ሴቶች በቦነሳይረስ ጎዳናዎች ላይ በእንባና በቁጣ የታጀበ ተቃውሞ ማድረጋቸውን አመልክቷል፡፡
ህጉ ውድቅ መደረጉን የተቃወሙ አርጀንቲናውያን የመኖራቸውን ያህል፣ ውሳኔውን ደግፈው በአደባባይ ደስታቸውን የገለጹ የጽንስ ማስወረድ ተቃዋሚ ዜጎች በርካቶች እንደሆኑም ዘገባው ገልጧል፡፡ በቅርቡ የተደረገ ጥናት፤ አብዛኛው የአገሪቱ ዜጋ የጽንስ ማስወረዱን እንደሚደግፍ ለማረጋገጥ መቻሉንም አስታውሷል፡፡
በአርጀንቲና የአምነስቲ ኢንተርናሽናል ዳይሬክተር ማሬላ ቤልስኪ፤ ረቂቅ ህጉን በተመለከተ ዜጎች የያዙትን አቋም ለመፈተሽ በተደረገው ጥናት፣ 60 በመቶ ያህል ዜጎች ህጉ እንዲጸድቅ እንደሚፈልጉ መግለጻቸውን አስታውሰው፣ ፓርላማው ህጉን ውድቅ ማድረጉ አግባብነት የለውም ሲሉ ተችተዋል፡፡
በአርጀንቲና የጽንስ ማቋረጥ ማድረግ የሚቻለው ሴቶች በአስገድዶ መድፈር ሲያረግዙና እርግዝናው ለእናትየዋ ጤና አስጊ ሲሆን ብቻ እንደሆነም ዘገባው አመልክቷል፡፡

•    ግልጽነትና አርኣያነት የጎደለው ምደባ በሚል እየተተቸ ነው
•    በተደጋጋሚ በጥፋት የተነሡ ሓላፊ፣ ለሦስተኛ ጊዜ ተመደቡ
•    በተደጋጋሚ ሕጸጽና ምዝበራ የታገዱት አስተዳዳሪም ተመለሰ

በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን የአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት፥ በሙስና፣ በአስተዳደር በደልና
በአሠራር ጥሰት የተካሔደውን ማጣራት ተከትሎ፣ 14 የዋና ክፍል ሓላፊዎች ከቦታቸው ቢነሡም፣ በምትካቸው የተደረገው ምደባ፣ ግልጽነትና አርኣያነት የጎደለው ነው፤ በሚል ቅሬታ አስነሣ፡፡ በቅዱስ ፓትርያርኩ መመሪያ በተቋቋመው ኮሚቴና የሰብአዊ መብት ኮሚሽንና የፌዴራል ጉዳዮች ሚኒስቴር
በታዛቢነት በተገኙበት ለአንድ ወር በተካሔደው ማጣራት፣ የአድባራት ካህናትንና ሠራተኞችን አላግባብ ከሥራ በማገድና በማሰናበት የሰብአዊ መብት ጥሰት እንደፈጸሙ ለቋሚ ሲኖዶስ ሪፖርት የቀረበባቸው የዋና ክፍል ሓላፊዎቹ እንዲነሡ መደረጉ ተገልጿል፡፡ ኾኖም፣ በቦታቸው ከተተኩት ሓላፊዎች መካከል የአንዳንዶቹ ምደባ፣ ከለውጡ ርምጃ ጋራ የማይጣጣም እንደኾነ ለአዲስ አድማስ አስተያየታቸውን የሰጡ አገልጋዮችና ሠራተኞች ገልጸዋል፡፡
ቀደም ሲል፣ ሓላፊነታቸውን አላግባብ ተጠቅመው በመዘበሩት የቤተ ክርስቲያኒቱ ገንዘብ ከፍተኛ የግል ሀብት
በማፍራትና አስተዳደራዊ በደል በማድረስ የታወቁ ግለሰቦች በተተኪነት መመለሳቸው፣ለቤተ ክርስቲያኒቱ አደጋ ነው፤ አገልጋዩንም ዋስትና የሚያሳጣ ነው፤ ሲሉ ስጋታቸውን ገልጸዋል - ሠራተኞቹ፡፡
“በሹም ሽረቱ የግብር ይውጣ ሥራ ተሠርቷል፤” የሚሉት ሠራተኞቹ፣ በ2007 ዓ.ም. በሀብት ብክነት፣
ሙስናና ሓላፊነትን በአግባቡ ካለመወጣት ጋራ ተያይዞ በቅዱስ ፓትርያርኩ መመሪያ ከሓላፊነታቸው ተነሥተውማጣራት እንዲካሔድባቸው የተወሰነባቸው የሒሳብና በጀት ዋና ክፍል ሓላፊ ሊቀ ጠበብት ኤልያስ ተጫነ፣ በአዲሱ ምደባ በዚያው ዋና ክፍል ለ3ኛ ጊዜ መሾማቸውን በመጥቀስ ምደባው ግልጽነትና አርኣያነት የሌለው ነው ሲሉ ተችተዋል፡፡ “በቂ ጥናት ሳይደረግና መመዘኛ መስፈርቱ ሳይታወቅ ወደ ሓላፊነት የመጡ ሰዎች ናቸው፤” የሚሉት አስተያየት ሰጪዎቹ፣ ከተተኩት መካከል፣ ከቀድሞዎቹ ጋራ የጥቅም ግንኙነት እንደነበራቸው የሚወቀሱም
በመኖራቸው፣ የሀገረ ስብከቱን የለውጥ ርምጃ የሚመጥን አፋጣኝ ማስተካከያ እንዲደረግ ጠይቀዋል፡፡
በቅርቡ ተካሒዶ በነበረው የቅዱስ ሲኖዶስ አስቸኳይ ስብሰባ፣ በሀገረ ስብከቱ አስተዳደራዊ መዋቅር ውስጥ፣
ሙስናን፣ ጥቅመኝነትንና የመልካም አስተዳደር ችግርን ለዘለቄታው የሚፈታ የአደረጃጀት ለውጥ እንዲደረግ
መግባባት ላይ ቢደረስም፣ የአስተዳደር ሓላፊዎቹ ምደባ ሒደቱን የሚያራምድ እንዳልኾነ ጠቁመዋል፡፡
ጥቅመኝነትን፣ ደላላነትንና ኑፋቄን ለማስወገድ ቃል ለገቡት የሀገረ ስብከቱ የወቅቱ ሥራ አስኪያጅም ፈተና
እንደሚኾንባቸው ቅሬታ አቅራቢዎቹ ስጋታቸውን ገልጸዋል፡፡
በሌላ በኩል፣ ከቦታቸው በተነሡት የዋና ክፍል ሓላፊዎች፣ አላግባብ ከሥራቸው ታግደውና ተሰናብተው
በአቤቱታ ላለፉት ሁለት ዓመታት ሲጉላሉ የቆዩት ካህናትና ሠራተኞች፣ ደረጃቸውና ጥቅማቸው ተጠብቆ ወደ
ሥራ ገበታቸው እንዲመለሱ መደረጉን የሀገረ ስብከቱ ሥራ አስኪያጅና የኢትዮጵያ ሰብአዊ መብት ኮሚሽን
በጋራ በሰጡት መግለጫ አስታውቀዋል፡፡ ታግደው በቆዩባቸው እስከ ሁለት ዓመታት ገደማ ያልተከፈላቸው
ወርኀዊ ደመወዝም ተሰልቶ እንዲከፈላቸው መወሰኑን ገልጸዋል፡፡
ኾኖም፣ ከታገዱት ሠራተኞች መካከል፥ በቀኖና ቤተ ክርስቲያን ጥሰት፣ በገንዘብ ምዝበራና በከፋ ምግባር
ተደጋጋሚ ጥፋት በመፈጸም ከሥራና ከደመወዝ እንዲታገዱ፣ ጉዳያቸውም በሊቃውንት ጉባኤ እንዲጣራ በቋሚ
ሲኖዶስ ውሳኔ የተላለፈባቸው ግለሰብ ወደ ደብር አስተዳዳሪነታቸው መመለሳቸው ተጨማሪ ቅሬታ ማስነሣቱ
ታውቋል፡፡ ከሃይማኖት ሕጸጽና ከሙስና ነጻ መኾናቸው እየታየ ወደ ሥራ እንዲመለሱ የተሰጠውን አቅጣጫ
እንደሚፃረርም ጠቁመዋል፡፡ እንዲህ ያለው አሠራር፣ በውሳኔው አስተማሪነት ላይ የሚኖረው አሉታዊ ተጽዕኖ
በቀላሉ የሚታይ ባለመኾኑ በአፋጣኝ ሊጤን እንደሚገባም አሳስበዋል - ተቺዎቹ፡፡
 


 ከጎረቤት አገራት በህገወጥ መንገድ እየገቡ ዜግነት የሚያገኙ ስደተኞች ያማረሩት የህንድ መንግስት፣ ሰሞኑን በወሰደው እርምጃ አሳም በተባለው የአገሪቱ ግዛት የሚኖሩ 4 ሚሊዮን ሰዎችን ዜግነት መንጠቁን ዘ ኢንዲፔንደንት ዘግቧል፡፡
ጎረቤት አገር ባንግላዴሽ ነጻነቷን ካወጀችበት እ.ኤ.አ ከ1971 አንስቶ በመቶ ሺዎች የሚቆጠሩ ባንግላዴሻውያን ወደ ግዛቱ በህገ ወጥ መንገድ እንደገቡ የጠቆመው የህንድ መንግስት፤ በቅርቡ ባደረገው ምርመራ ዜግነታቸውን የሚያረጋግጥ ህጋዊ ሰነድ የሌላቸው 4 ሚሊዮን ሰዎች ማግኘቱን አመልክቷል፡፡
እነዚሁ 4 ሚሊዮን ሰዎች ህንዳውያን መሆናቸውን የሚያረጋግጥ የሰነድ ማስረጃ እስከ መስከረም ወር መጀመሪያ ድረስ ለሚመለከተው የመንግስት አካል በማቅረብ ዜግነታቸውን እንዲያረጋግጡ ጥሪ ቀርቦላቸዋል ያለው ዘገባው፤ እስከዚያው ድረስ ግን ህገወጥ ስደተኛ ተብለው እንደማይመዘገቡ ቃል እንደተገባላቸው አመልክቷል፡፡

 ታዋቂው ፎርብስ የ2018 የፈረንጆች አመት የአለማችን ከፍተኛ ተከፋይ 100 ዝነኞች ዝርዝር ይፋ ያደረገ ሲሆን፣ አሜሪካዊው የከባድ ሚዛን ቦክስ ሻምፒዮናው ሜይዌዘር በ285 ሚሊዮን ዶላር ቀዳሚነቱን ይዟል፡፡
የኦስካር ተሸላሚው ታዋቂው የፊልም ተዋናይ ጆርጅ ክሉኒ ባለፉት 12 ወራት ከታክስ በፊት 239 ሚሊዮን ዶላር ገቢ በማግኘት የሁለተኛ ደረጃን ሲይዝ፣ የሪያሊቲ ሾው አዘጋጇ ኬሊ ጄኔር በ166.6 ሚሊዮን ዶላር ሶስተኛ ደረጃ ላይ ተቀምጣለች፡፡
ፎርብስ ለ22ኛ ጊዜ ይፋ ባደረገው አመታዊው የአለማችን ከፍተኛ ተከፋይ ዝነኞች ዝርዝር ውስጥ የተካተቱት የዘንድሮ 100 ከዋክብት በድምሩ 6.3 ቢሊዮን ዶላር ገቢ ማግኘታቸው የተነገረ ሲሆን፣ ዝነኞቹ ከ17 የአለማችን አገራት የተውጣጡ ናቸው ተብሏል፡፡
በዘንድሮው የፎርብስ ከፍተኛ ተከፋይ የአለማችን ዝነኞች ዝርዝር ውስጥ ከስፖርቱ ዘርፍ የተመረጡትን ክርስቲያኖ ሮናልዶና ሊዮኔል ሜሲን ጨምሮ፣ በሙዚቃ፣ በፊልም፣ በሚዲያና በሌሎች የተለያዩ መስኮች የሚታወቁ ከዋክብት መካተታቸውም ተነግሯል፡፡

 ሳምሰንግ በሽያጭ ሲመራ፣ አፕል ቦታውን ለሁዋዌ አስረክቧል

    ታዋቂው የቻይና ኩባንያ ሁዋዌ በአለማችን የስማርት ሞባይል ቀፎዎች ገበያ በርካታ ምርቶችን በመሸጥ በአፕል ተይዞ የቆየውን የ2ኛነት ደረጃ መረከቡን ሲኤንቢሲ ኒውስ ዘግቧል፡፡
የቻይናው ሁዋዌ እስካለፈው ሰኔ በነበሩት ሶስት ወራት ጊዜ ውስጥ በአለማቀፍ ደረጃ 54.2 ሚሊዮን ሞባይሎችን መሸጡንና በአለማቀፍ ገበያ ውስጥ የ15.8 በመቶ ድርሻን መያዙን የጠቆመው ዘገባው፤ የታዋቂው አይፎን አምራች የሆነው አፕል ኩባንያ በአንጻሩ 41.3 ሚሊዮን ሞባይሎችን በመሸጥ የ12.1 በመቶ የገበያ ድርሻ መያዙን አመልክቷል፡፡
የደቡብ ኮርያው ሳምሰንግ ኩባንያ በአለማቀፍ የሞባይል ሽያጭና የገበያ ድርሻ መሪነቱን ይዞ መቀጠሉን የጠቆመው ዘገባው፤ በተጠቀሱት ሶስት ወራት ጊዜ ውስጥ 71.5 ሚሊዮን የተለያዩ አይነት የሞባይል ቀፎዎችን በመሸጥ በአለማቀፉ የሞባይል ገበያ ውስጥ የ20.9 በመቶ ድርሻውን መያዙን ገልጧል።

 ጅቡቲ፤ የሱማሌው ፕሬዚዳንት ሞሃመድ አብዱላሂ ሞሃመድ፣ በኤርትራ ላይ የተጣለው ማዕቀብ እንዲነሳ ባለፈው ሳምንት ለተባበሩት መንግስታት ድርጅት ያቀረቡትን ጥያቄ በጽኑ መቃወሟን ቪኦኤ ዘግቧል፡፡
የሱማሌው ፕሬዚዳንት ሞሃመድ አብዱላሂ ሞሃመድ ባለፈው ሳምንት በኤርትራ የሶስት ቀናት የስራ ጉብኝት ማድረጋቸውን ያስታወሰው ዘገባው፤ ፕሬዚዳንቱ በጉብኝታቸው ወቅት የተባበሩት መንግስታት ድርጅት የጸጥታው ምክር ቤት እ.ኤ.አ በ2009 በኤርትራ ላይ የጣለውን የኢኮኖሚና የጦር መሳሪያዎች ማዕቀብ እንዲያነሳ ጥሪ ማቅረባቸው ጅቡቲን ክፉኛ ማስቆጣቱን አመልክቷል፡፡
በጅቡቲ የሶማሊያ አምባሳደር አደን ሃሰን፤ “የሶማሊያው ፕሬዚዳንት ለተመድ ያቀረቡት የማዕቀብ ይነሳ ጥያቄ እጅግ አስደንግጦናል፣ በጽኑም እንቃወመዋለን” ሲሉ መናገራቸውን የጠቆመው ዘገባው፤ “ኤርትራ የይገባኛል ውዝግብ ያለባቸውን የሩሜራ ደሴቶችን ያላግባብ ይዛብናለች፣ ከአስር በላይ ዜጎቻችንንም በእስር ቤት እያሰቃየችብን ነው፣ ስለዚህም ተመድ የጣለባት ማዕቀብ ሊነሳላት አይገባም” በሚል ተቃውሟቸውን ማሰማታቸውንም ገልጧል፡፡
“ሶማሊያ በአካባቢው ካሉ ጎረቤት አገራት ጋር ዲፕሎማሲያዊ ግንኙነትን የማጠናከር ህጋዊ መብት ቢኖራትም፣ የረጅም ዘመናት ወዳጃችን የሆነቺው ሶማሊያ ሉአላዊ ግዛታችንን ለወረረቺውና ዜጎቻችንን በእስር ለምታሰቃየው ኤርትራ እንዲህ አይነት ድጋፍ ማድረጓን መንግስታችን በጽኑ ይቃወመዋል” ማለታቸውንም ዘገባው አመልክቷል፡፡

 ከዕለታት አንድ ቀን አንድ አዳኝ ሰው ወፎች እያጠመደ ይኖር ነበር፡፡ አንድ ቀን አንዲት የወርቅ ቀለም ያለው ላባ ያላት ወፍ አጠመደ፡፡ ለብዙ ቀናት የወፍ መኖሪያ መረብ ሰርቶ ምግብ እያከማቸና እየቀለበ ካስቀመጣት በኋላ አንድ ቀን፤
“ወፌ ሆይ! እስከዛሬ ስቀልብሽ እንደነበርኩ ታስታውሻለሽ፣ አይደል?” አለና ጠየቃት፡፡
ወፊቱም፤
“አዎን ጌታዬ! ተንከባክበህ፣ አሳምረህ አኑረኸኛል፡፡ ወደፊትም ታኖረኛለህ የሚል ሙሉ ዕምነት አለኝ!” ስትል መለሰች፡፡
“ግን ወፌ!” አለና ጀመረ አዳኙ ጌታዋ፤ “አሁን ሁለት ነገር ለማድረግ እፈልጋለሁ፡፡ ሁለተኛው የወርቅ ላባሽን መሸጥና መጠቀም ነው፡፡ የመጀመሪያው ደግሞ ላባሽን በቁምሽ መንጨትና መሸጥ ስለማልፈልግ፤ አርጄ እበላሻለሁ፡፡ ከዚያ ላባሽን እሸጠዋለሁ! ሌላ ምንም ለማድረግ አልችልም!” አላት፡፡
ወፊቱ ጥቂት ካሰበች በኋላ፤
“ጌታዬ ሆይ! ያልከው ዕውነት ነው፡፡ ሆኖም አንተ ካሰብከው በላይ ጠቃሚ የሆነ ነገር እሰጥሃለሁ”
“ምን?” አለ ጌትየው፡፡
“አየህ፤ የእኔን ሥጋ መብላትም ሆነ የወርቅ ላባዬን መሸጥ ያለው ጥቅም የአንድ ጊዜ ብቻ ነው፡፡ እኔ የምሰጥህ ነገር ግን ዘለዓለም የምትጠቀምበት ነው፡፡”
“ምንድን ነው የምትሰጪኝ?”
“ምክር”
“ምን ምክር?” አለ በጉጉት፡፡
“ሦስት ምክሮችን ነው የምለግስህ፡፡ አንደኛውን እዚሁ እጅህ ላይ ሳለሁ እነግርሃለሁ፡፡
ሁለተኛውን አቅራቢያችን ካለው ዛፍ ላይ ሆኜ እነግርሃለሁ፡፡ ሦስተኛውን አየር ላይ ሆኜ አበስርሃለሁ።”
አዳኙ በሀሳቧ ተስማማና፤
“እሺ፤ የመጀመሪያውን ንገሪኝ” አላት፡፡
ወፊቱም፤ “የመጀመሪያው ምክሬ፤ የማታገኘውን ነገር አትመኝ! የሚል ነው”
አዳኙም፤ “ጥሩ፤ ሁለተኛውን ንገሪኝ” አለና ወደ ዛፉ እንድትሄድ ለቀቃት፡፡
ወፊቱም እየበረረች ዛፉ ላይ አረፈች፡፡ ከዚያም፤ “በእጅህ የገባውን ነገር በጥንቃቄ ያዝ፤ አትልቀቅ” ብላው ወደ አየር ከነፈች፡፡
ይሄኔ አዳኙ በጣም ተናዶ፤
“ወይኔ! ወይኔ! አንቺን መልቀቅ አልነበረብኝም፡፡” እያለ ፀጉሩን ሲነጭ፤
“አሁን ሶስተኛውን ምክሬን ልንገርህ” አለችና ከንዴት አስቆመችው፡፡
“ሦስተኛውን ምክርሽን ልስማ እሺ?” አለ፡፡
ወፊቱም፤
“ባለፈ ነገር አትፀፀት” ብላ ወደ ህዋ አንደኛዋን መጠቀች፡፡
***
የወፊቱ ምክሮች በአሁኑ ወቅት ለእኛ የሚሆኑ ናቸው፡፡ የማናገኛቸውን ነገሮች መመኘት አይኖርብንም። የምንመኘውን ነገር ለማግኘት አቅማችንን፣ ጊዜውንና አካሄዳችንን ከምር ማስላትና ማውጠንጠን አለብን። አለበለዚያ፤
“ምኞቴ እንደጉም መንጥቃ
ተስፋዬ እንደጉድፍ ወድቃ
የወንድሜን ልጆች እንኳ፣ ላባት ርስት ሳላበቃ
የእኔ ነገር በቃ በቃ …” ብለን እንቀራለን (ፀጋዬ ገ/መድህን፣ የከርሞ ሰው፤ አብዬ ዘርፉ)
ቀጥሎ በልቦናችን ሊመዘገብ የሚገባው፣ በእጃችን ያለውን አጥብቀን መያዝን ነው፡፡ ኢትዮጵያ በጀመረችው የለውጥ ጉዞ እያገኘችና እያስመዘገበች ያለው ድል የእስካሁን ዕድሜው አጭር ከመሆኑ በስተቀር አመርቂና ዘላቂ እንደሚሆን፣ ተስፋው እጅግ ያማረ ነው! ይህንን ድል መጠበቅና ተጠንቅቆ መያዝ ተገቢ ነው!! ምነው ቢሉ፤ አንሸራታች ደለልና “ያፋፍ ላይ ድጥ” መቼም ቢሆን ሊያጋጥም ይችላልና! በመሰረቱ፤ ማናቸውም ወደፊት የሚጓዝ ክስተት ከአሮጌ ሥርዓት ጋር መጋጨቱም ሆነ፤ ግራ የተጋባው የህብረተሰብ ክፍል መንገዱና መንፈሱ ሲያቀዣብረው፤ እንደ ተራ ምቀኝነትም ራሱ የሌለበት ነገርና ያልቃኘው ክራር የማይጥመው ወገን መኖሩ፤ ከቶም አስገራሚ አይደለም! እኒህን “የአውቆ አበድም ሆነ የአብዶ - አወቅ” ክፍሎች ወይም ወቅትን በወግ በወጉ አድርገው ለመጠቀም ያልቻሉ ወገኖችን፤ አግባብና ጥንቃቄ ባለው አያያዝ ማቀፍ ብልህነት ነው!
ማንም ጅል የማይስተው ጉዳይ ግን፣ አመራር የሆነ አካል ከጥበብና ከብልሃት ውጪ በሌላ ጎርበጥባጣ ፖለቲካዊ መንገድ እፈታዋለሁ ማለት ዘበት እንደሆነ ነው! ቀሳውስቱን፣ ምሁር ዳያስፖራውን፣ ተቃዋሚውንና በምንም ሰበብ ከሀገር የወጣውን ዜጋ ወደ ቤቱ፣ ወደ ቀዬው፣ ወዳገሩ ሊመልስ የሚችል ዕውቀት፣ ጥበብና ፍቅር ካለን፤ የውስጥ ቅራኔን ለመፍታት እንዴት መላ እናጣለን?! በእጃችን የያዝነውን እናጥብቅ!!
ሶስተኛው ወፋዊ ምክር፡- ባለፈ ነገር አለመፀፀት ነው፡፡ ከትላንትና መላቀቅ! በዕውቀት ያለፈውን መፍታት!!፡፡ ሀገራዊ ዕርቅን በጥንቃቄ ማስፋፋት!! ነገን መሻማት፡፡ ቢቻል ከነገ መስረቅ! (Plagarizing the future)
ዛሬ የኢትዮጵያን ለውጥ ለማምጣት በሚደረገው ሙከራ ውስጥ አንዱ ዓይነተኛ ተግባር ከአናት የተቃኘ ዲሞክራሲን ማስወገድ ነው (Guided democracy እንዲሉ)፡፡ እስካሁንም ዲሞክራሲያዊ አካሄድ እንዲሽመደመድ ያደረገው፤ “ይሄው በልካችሁ የተሰፋ ዲሞክራሲ እኔ ልስጣችሁ” የሚል አባዜ ነው፡፡ ከወዲሁ የከረረውን የማላላት፣ ፅንፍ ይዞ የሚጓዘውን ሃይ የማለት፣ ተቋሚነትን በህብረተሰብ ተሳትፎ የመገንባት ጠንካራ ስራ ይጠብቃል፡፡ ህዝብ “ጉዳዩ የእኔ ነው” እንዲል፣ ውሎ አድሮም የፈረሱን ልጓም እንዲጨብጥ ማድረግ ቀዳሚ እሳቤ መሆን ይኖርበታል፡፡ “እኔ ነኝ ያደረኩለት ዓይነት” አመለካከት፣ ህዝብ አያውቅም ወደሚል ክፉ ግምት ስለሚጥል አደገኛ ነው፡፡ አለበለዚያ፤ በ“እናት ዓለም ጠኑ” የፀጋዬ ገ/መድህን ቴያትር ውስጥ ተውኔታዊ ግነት ባለው መልኩ እንደቀረበውና ገራፊው ገብረየስ ጅሉ ሞሮን፤ “ዕድሜ ለእኔ በል፣ እሥር ቤት ውስጥ እኔ ስገርፍ እያየህ ከአንድ እስከ አርባ ቁጥር ተማርክ” የሚለውን ምፀታዊ አነጋገር ዕውን ከማድረግ የማይተናነስ ስህተት እንፈፅማለን፡፡ ከዚህ ይሰውረን!

የዲሞክራቲክ ሪፐብሊክ ኮንጎ መንግስት 33 ዜጎችን ለህልፈተ ህይወት የዳረገው የኢቦላ ቫይረስ ወረርሽኝ በቁጥጥር ስር መዋሉን ይፋ ባደረገ በቀናት ዕድሜ ውስጥ ቫይረሱ በአገሪቱ ዳግም በወረርሽኝ መልክ መከሰቱ ተዘግቧል፡፡
የአገሪቱ የጤና ሚኒስትር ከትናንት በስቲያ የሰጡትን መግለጫ ጠቅሶ ዘ ጋርዲያን እንደዘገበው፣ በዲሞክራቲክ ሪፐብሊክ ኮንጎ ሰሜን ምስራቃዊ አካባቢ በምትገኘው የኪቩ አውራጃ የተቀሰቀሰው የኢቦላ ቫይረስ ወረርሺኝ አራት ሰዎችን ማጥቃቱ ተረጋግጧል፡፡
በአውራጃዋ ባለፈው ቅዳሜ 20 ሰዎችን ለህልፈተ ህይወት የዳረገ በሽታ መታየቱን ተከትሎ በተደረገው ምርመራ፣ አራት ሰዎች በኢቦላ ቫይረስ መጠቃታቸውን ለማረጋገጥ መቻሉን የጠቆመው ዘገባው፣ በአዲስ መልክ የተቀሰቀሰው የኢቦላ ወረርሺኝ በቅርቡ ተከስቶ ከነበረውና ባለፈው ሳምንት በቁጥጥር ውሏል ተብሎ ከተነገረለት ወረርሺኝ ጋር ግንኙነት ይኑረው አይኑረው የተረጋገጠ ነገር የለም ብሏል፡፡
የአለም የጤና ድርጅት በአዲስ መልክ የተቀሰቀሰውን የኢቦላ ወረርሽኝ ለመግታት በአፋጣኝ የህክምና ባለሙያዎች ግብረ ሃይል ማቋቋሙንና ከአገሪቱ መንግስት ጋር እርብርብ ማድረግ መጀመሩንም ዘገባው አመልክቷል፡፡
ኢቦላ ለዲሞክራቲክ ሪፐብሊክ ኮንጎ በቀላሉ የማታሸንፈውና በቋሚነት ፈተናዋ ሆኖ የሚቀጥል አገራዊ ተግዳሮት ነው ያሉት የአለም የጤና ድርጅት ዳይሬክተር ዶክተር ቴዎድሮስ አድሃኖም፤ የአገሪቱ መንግስትና የጤናው ዘርፍ ባለሙያዎች ለችግሩ መፍትሄ ለመሻት ቀጣይነት ያለው እርብርብ እንዲያደርጉም ጥሪ አቅርበዋል፡፡

 ለአርእስትነት የተመረጠው አባባል የሴቶች ጤንነትን በሚመለከት በአዲስ አበባ ተደርጎ በነበረ አንድ መድረክ በተበተነ አጀንዳ ላይ መሪ ሐሳብ ሆኖ የቀረበ ነው፡፡ የሴቶችን ጤና በመጠበቁ ረገድ በተለይም የጤናው ዘርፍ ባለሙያዎች በምን መልኩ ዛሬም ነገም ከእሱዋ ጋር መሆን እንደሚጠበቅባቸው የሚያሳዩ ሳይንሳዊ ጽሁፎች የቀረቡበት ነበር፡፡ ሐምሌ 5/2010 በራድሰን ብሉ ሆቴል ለአንድ ቀን በቅዱስ ጳውሎስ ሚሊኒየም ሜዲካል ኮሌጅ እና በኢትዮጵያ የጽንስና ማህጸን ሐኪሞች ማህበር Roche በተባለ የውጭ ድርጅት አማካኝነት ለአ ንድ ቀን በተደረገው የግንዛቤ ማስጨበጫ ፕሮግራም አንዱ አባባል ዛሬ መስራት ታካሚዎች ነገ የሚፈልጉትን ነገር ለማሟላት ይጠቅማል የሚል ሀሳብ ነበረው። በእለቱ ከተነሱት ነጥቦች መካከል መካንነትና የማህጸን ካንሰርን በሚመለከቱ ርእሶች ላይ የተደረጉ ጥናቶች እና እውነታዎች በባለሙያ ዎች ቀርበዋል፡፡ በዚህ እትም ለንባብ ያቀረብነው በተለይም በማህጸን በር ካንሰር ዙሪያ ያለውን ሀሳብ ሲሆን በዚህ ርእሰ ጉዳይ ዶ/ር ታደሰ ኡርጌ የጽንስና ማህጸን ሕክምናና የመራቢያ አካላት ካንሰር ሕክምና እስ ፔሻሊስትን ከቅዱስ ጳውሎስ ሆስፒታል ሚሊኒየም ሜዲካል ኮሌጅ አነጋግረናል፡፡
እንደ ዶ/ር ታደሰ እማኝነት በዚህ በአንድ ቀን የግንዛቤ ማስጨበጫ ውሎ የተነሱ አበይት ጉዳ ዮች ሁለት ናቸው፡፡ እነሱም መካንነት እና የማህጸን በር ጫፍ ካንሰር ዙሪያ ያሉ አሰ ራሮ ችንና አዲስ ቴክኖሎጂን የማስተዋወቅ እና ወደ አፈጻጸሙም እንዴት መግባት እንደሚቻል የተጠቆመ በት ነበር፡፡ በቀጥታ ከእኔ ሙያ ጋር በተያያዘ ማንሳት የምፈልገው ከማህጸን ጫፍ ካንሰር ጋር የተያያዘውን ይሆናል በማለት ዶ/ር ታደሰ የሚከተለውን ማብራሪያ ሰጥተዋል፡፡
የማህጸን በር ወይንም ጫፍ ካንሰር መከላከል የምንችለው የካንሰር አይነት ነው፡፡ ካንሰሩ ሳይከሰት አስቀድሞ በምርመራ ወደ ካንሰር የመሄዱን ሁኔታ ማወቅ ስለሚቻል ሕክምናውን በመስጠት ካንሰሩን ለማስቆም የሚያስችል አሰራር አለ፡፡
ዶ/ርታደሰ አያይዘው እንደገለጹትም የማህጸን ጫፍ ካንሰር መከላከል ከሚቻሉ የካንሰር አይነቶች አንዱ ነው፡፡  የቅድመ ካንሰር ምርመራ ዘዴዎች የተለያዩ ናቸው፡፡ ስለሆነም ባደጉት አገራት ያለው የምርመራ ዘዴ የተለያየና ዘመናዊነቱም ከፍ ያለ ሲሆን በእኛ አገር ግን ዝቅተኛ በሆነ ወጪ በየትኛውም የመንግስት ጤና ተቋም ደረጃ (VI ) visual Inspection በሚባለው ምርመራውን ሰርቶ ችግሮች ሲኖሩ ማከም የሚቻልበትን ዘዴ የኢትዮያ የጤና ጥበቃ ሚኒስቴር ቀርጾ ወደ ስራው የተገባበት ነው ፡፡  በእርግጥ እኛ የምንጠቀምበት ምርመራ ምን ያህል ጠቀ ሜታዎች አሉት ወይንም ምን ያህል በትክክል ችግሩን በምርመራው አውቆ ሰዎቹን መርዳት ያስችላል ስለሚለው ብዙ ነገር ያለ ሲሆን ነገር ግን በዋናነት ተመራጭ ሆኖ ሳይሆን ከወጪ ጋር ተያይዞ የሚተገበር ነው፡፡ ከወጪም ብቻ ሳይሆን ከሰው ኃይል እንዲሁም ከአቅርቦት አቅም ጋር በማያያዝ ካንሰር ከመከላከል አንጻር ሲታይ የራሱ ችግሮች ቢኖሩትም እንኩዋን ውጤታማ በመሆኑም ነው፡፡
የማህጸን በር ካንሰርን በመከላከል ረገድ ሌሎች ማለትም ኢትዮጵያ ውስጥ ጥቅም ላይ ከሚው ለው በተሻለ አገልግሎት ላይ የሚውሉ የቴክኖሎጂ ዘዴዎች አሉ፡፡ ለምሳሌም ፡-
ሳይኮሎጂ የሚ ባል ወይንም ሴሎችን ከማህጸን ጫፍ ላይ ወስዶ መመርመር፤
ሌላው አሁን በመለመድ ላይ ያለው የ (HPV)DNA ምርመራ ማለትም ይህንን የማህጸን ጫፍ ካንሰር የሚያመጣ ሕዋስን መመርመር ማለት ነው፡፡
በዚህ ቫይረስ ያልተጠቁ ሴቶች ይህ በሽታ ሊይዛቸው ስለማይችል ብዙ ሴቶችን ይህ ምርመራ ይረዳል፡፡ ስለዚህ ከሌላው ሁሉ ይህ የተሻለ ቴክኖሎጂ ነው፡፡ ከምርመራው ሁኔታ ጀምሮ በምን ያክል ጊዜ መመርመር አለባቸው ?ቫይረሱ ካለባቸው ምን መደረግ አለበት ?ቫይረሱ ከሌለባቸ ውስ ?የሚለውን ሁሉ የያዘ የግንዛቤ ማስጨበጫ መድረክ ነበር እንደ ዶ/ር ታደሰ ኡርጌ ማብራሪያ፡፡ ይህ ዘመናዊ የምርመራ ሂደት በተለይም ዋጋው ከበድ የሚል ነው በሚል ብዙ አገራት ኢትዮ ጵያን ጨምሮ የማይደፍሩት ቢሆንም እንደ ሰብሳቢዎቹ እማኝነት ግን በእርግጥ አንዲት ሴት ለአንድ ጊዜ በምታደርገው ምርመራ ውድ ነው ሊባል ቢችልም ነገር ግን አንዲት ሴት እስከ 65/አመት እድሜዋ ድረስ ልታደርገው ከሚገባት ምርመራ አንጻር ሲታይ ግን ዋጋው ውድ ነው አይባልም፡፡ በዚህ የምርመራ ዘዴ አንዴ ተመርምረው ቫይረሱ የሌለባቸው ከሆነ ለረጅም ጊዜ ሳይመረመሩ መቆየት ይችላሉ፡፡ አንዳንዴም ቫይረሱ ሳይኖርባቸው አንዳንድ ለውጥ ሲከሰት በሌላ ምርመራ ሊገኝ ስለሚችል ይህም ወጪ ያስከትላል፡፡በሌላ በኩል ደግሞ ቫይረስ እያለባቸው ነገር ግን ሳይታወቅና በሁዋላም ቫይረሱ ሊከሰት እየቻለ ግን ሳይታከም ቢቀር ለሚደረገው ሕክምና የሚወጣው ወጪም ሲሰላ ከበድ ማለቱ አይቀርም፡፡ ስለዚህም እንደነዚህ ያሉትን ነገሮች ስንመረምር በረጅም ጊዜ ሂደት ያለው የዋጋ ውድነት ከአዲሱ ቴክኖሎጂ የሚበልጥ ሳይሆን እንዲያውም የሚያንስ ነው የሚል የግንዛቤ ማስጨበጫ ነጥብ ተነስቶአል፡፡  
የግንዛቤ ማስጨበጨው መድረክ ለተሳታፊዎች በበተነው መረጃ ላይ እንደሚታየው፡-
በአለማችን በየአመቱ ወደ 530.000/የሚጠጉ አዲስ የማህጸን በር ካንሰር ታማሚዎች ይከሰታሉ፡፡
ሰርቫይካል ካንሰር በጊዜው ከታከመ ከ80% በማያንስ ሁኔታ የሚድን በሽታ ነው፡፡
ይሁን እንጂ በአለም አቀፍ ደረጃ በየአመቱ ወደ 270.000/የሚሆኑ ሴቶች በማህጸን በር ካንሰር ምክንያት ለሕልፈት ይዳረጋሉ፡፡
ATHENA የተባለው ጥናት እንደሚያሳየው አብዛኛው ሕመም ከ40/አመት በላይ ካሉት ጋር ሲነጻጸር ከ25-29/ አመት እድሜ በሚገመቱ ሴቶች ላይ ይበዛል፡፡
ዶ/ር ታደሰ እንደሚሉት አሁን በአገራችን በተለይም በመንግስት ሆስፒታሎች የሚደረገው የቅድመ ካንሰርም ሆነ ካንሰሩ ከተከሰተ በሁዋላ የሚደረገው ምርመራ ብዙ ሕመምተኞችን እያገዘ ይገኛል። በግንዛቤ ማስጨበጨው መድረክ ላይ የተነሳው አዲስ ቴክኖሎጂ ደግሞ የቫይ ረስን DNA መመርመርን የሚጠይቅ ነው፡፡ ስለዚህም አሁን እየተደረገ ያለው አዲስ ሳይንሳዊ ውጤቶች ሲኖሩ ቀድመው ወደስራው የተሰማሩ ሐኪሞችን ግንዛቤው እንዲኖራቸው ማድረግ፤ የተሻለ ከሆነና ባለሙያው ነገሩ ከገባው በተለይም ይጠቅማል ብሎ ካሰበ ወደ ሐገር እንዲገባ የተለያዩ መንገዶችን መፈለግ፤ ጥያቄ ማቅረብ፤ የመሳሰሉት ነገሮች  እንዲከሰቱ  ማድረግ እንዲያስችል ነው፡፡ ከዚህም በተጨማሪ ይህን መመርመሪያ መሳሪያ ወደአገር ለማስገባት የሚያስችል አቅም ያላቸው ድርጅቶችም ስለሁኔታው እንዲያስቡ ለማድረግ ያስችላል፡፡
በአሁኑ ወቅት ኢትዮጵያ ውስጥ ያለው የምርመራ ሁኔታ ከላይ እንደተገለጸው (VI) visual Inspection የሚባለው ነው፡፡ ነገር ግን በዚህ የሕክምና ዘርፍ ሳይንሱ የትጋ ደርሶአል? የት ኛው ይሻላል? ለሚለው ጥያቄ የተለያዩ ጽሁፎችን ወይንም ጥናቶችን…ወዘተ ከማንበብ በተጨ ማሪ ቴክኖሎጂውን በትክክል በሚያውቁት እንደነዚህ ባሉ ባለሙያዎች የግንዛቤ ማስጨበጫ ፕሮግራም መዘጋጀቱ በጣም ጠቃሚ ነው፡፡ በሌላም በኩል ይህ ነገር በትክክል ለኛ ይጠቅማል ወይንስ ?የሚለውንና ለምርምር መነሻ የሚሆኑ ሀሳቦችንም አንስቶ መወያየት ፤የፖሊሲ አቅጣጫንም መፈተሸ የባለሙያው ድርሻ ስለሆነ ከዚህ የሚገኘው ውጤት በቀጣይ ለሚኖሩት ታካሚዎች አገልግሎት አሰጣጥ አስፈላጊ ነው፡፡
ዶ/ር ታደሰ ከጽንስና ማህጸን ሕክምና እስፔሻሊስትነት በተጨማሪ Gynecology oncologist በተባለው የሙያ ዘርፍ  በተለየ እስፔሻሊስትነት ተምረው የመራቢያ አካላትን ካንሰር በመከላ ከልና በማከም ረገድ በአሁኑ ወቅት በቅዱስ ጳውሎስ ሆስፒታል በመስራት ላይ ይገኛሉ፡፡ የት ምህርቱን መጀመር አስመልክተን ባነጋገርናቸው ወቅት እና በአሁኑ ጊዜ ያለውን የታካሚ ሁኔታ ሲገልጹ በጳውሎስ ሆስፒታል ደረጃ ሲታይ ያለው የህመምተኛ ቁጥር እየጨመረ ነው፡፡ ቀደም ሲል ስራው ሲጀመር በሳምንት አንድ ቀን በሚኖረው የክሊኒክ ሕክምና በጣም ጥቂት ምናልባትም 4/ እና 5/ ሰዎች ለምርመራ ይቀርቡ ነበር፡፡ አሁን ግን በሳምንት ከ50/በላይ ሕመ ምተኞችን እናያለን፡፡ ይህም የሚሆንበት ምክንያት የካንሰር ሕክምና በአንድ ጊዜ የሚያበቃ ሳይሆን ቀጣይነት ያለው በመሆኑም ነው፡፡ ይህ እንግዲህ በጥቅሉ የመራቢያ አካላት ካንሰርን የሚመለከት ሲሆን ከዚህ ውስጥ አንዱ የማህጸን በር ጫፍ ካንሰር ነው፡፡ ስለዚህም አንዳንዶች የካንሰሩ ይዘት በዚህ ሆስፒታል ከሚታይበት ደረጃ ላይ ካልሆነ ለምሳሌም ካንሰሩ ወደ ሽንት ፊኛ ወይንም ወደአጎራባች አካላት ላይ የመታየት አዝማሚያ ካለ  እና የጨረር ሕክምና ካስፈ ለገ ዛሬም ወደጥቁር አንበሳ ሆስፒታል ይላካሉ፡፡ ግን አሁን በግንዛቤ ማስጨበጫው ፕሮግ ራም ያየነው በሽታ አምጪ ሕዋስ ሳይኖር ወይንም ጉዞውን ሳይጀምር ማለትም ወደፊት ካን ሰር ከ10-15/ አመት ባለው ጊዜ ሊመጣ ይችላል የሚያሰኘውን በሽታ አስቀድሞ ለማስቀረት ውጤታማ የሆነ ቴክኖሎጂ ነው፡፡ ግን አሁንም አገሪቱ በምትችለው አቅም የማህጸን በር ካንሰ ርን መከላከል ስለሚቻል በስራ ላይ ያለውን ቴክኖሎጂ መጠቀም የሁሉም ምርጫ መሆን አለ በት፡፡ ከዚህ ባለፈ ግን በመንግስት ተቋማት ሳይሆን በግሉ ዘርፍ መሳሪያው ሊኖር ስለሚ ችል የሚፈልጉ አጠያይቀው መጠቀም ይችላሉ ዶ/ር ታደሰ ኡርጌ እንደገለጹት፡፡

 በልዩነቱ ያዘኑ ምእመናንን ይቅርታ ለመጠየቅ ተወስኗል
          “ዋነኛው የጥላቻ ምሶሶ በይፋ ተናደ”/ጠቅላይ ሚኒስትሩ/


    ላለፉት 26 ዓመታት በተፈጠረ አለመግባባት ለሁለት ተከፍሎ የነበረው የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ቅዱስ ሲኖዶስ ወደ አንድነቱ እንዲመለስ እንዲሁም ቤተ ክርስቲያኒቱ በሁለት ፓትርያርኮች እንድትመራ ከስምምነት ተደረሰ፡፡
ካለፈው ሳምንት እሑድ ጀምሮ በአሜሪካን ዋሽንግተን ዲሲ የተካሔደው የኢትዮጵያውና የአሜሪካኑ ሲኖዶሶች የሰላም ጉባኤ በዕርቅ መቋጨቱን ተከትሎ፣ ቤተ ክርስቲያኒቱ፣ ጠቅላይ ሚኒስትር ዶ/ር ዐቢይ አሕመድ በተገኙበት አንድነቷን ከትላንት በስቲያ ሐምሌ 19 ቀን ዐውጃለች፡፡
4ኛው ፓትርርክ ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ መርቆሬዎስ፣ በ1984 ዓ.ም. በፖለቲካዊ ግፊትና ጫና መንበራቸውን ለቀው ከተወሰኑ ብፁዓን አባቶች ጋራ መሰደዳቸውን ተከትሎ፣ የአሜሪካው የስደት ሲኖዶስ እና የኢትዮጵያው የሀገር ቤቱ ሲኖዶስ በሚል በተፈጠረ መከፋፈል ቀኖና እንደተጣሰና አስተዳደራዊ ልዩነት እንደተከሠተ ተገልጿል፡፡
ከሁለቱ ሲኖዶሶች የተወከሉ ስድስት ልኡካን አባቶች፣ባለፈው ሰኞ ሐምሌ 16 ቀን ያለአደራዳሪ በቀጥታ ባካሔዱት የአጭር ጊዜ ውይይት፣ መከፋፈሉ እንዲያበቃ ከስምምነት መድረሳቸው ተበሥሯል፡፡ ላለፉት 26 ዓመታት የዘለቀው ልዩነት አብቅቶ ቤተ ክርስቲያኒቱ ከአንድ ቅዱስ ሲኖዶስ መመሪያ እየተቀበለች እንደምትመራ ከትላንት በስቲያ ሐምሌ 19 ቀን፣ በጋራ ባወጡት መግለጫ አስታውቀዋል፡፡
በዚሁ ባለ6 ነጥቦች መግለጫ መሠረት፣ ላለፉት 26 ዓመታት በስደት በአሜሪካ የኖሩት ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ መርቆሬዎስ፣ በፓትርያርክ ማዕርግ ወደ ኢትዮጵያ ተመልሰው በመንበረ ፓትርያርኩ በሚዘጋጅላቸው ለክብራቸው የሚመጥን ማረፊያ ይቀመጣሉ፡፡ሁለቱም ቅዱሳን ፓትርያርኮች የሥራ ድርሻ እንደሚኖራቸው በመግለጫው ተጠቅሷል፡፡ 4ኛው ፓትርያርክ ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ መርቆሬዎስ፣ በጸሎትና በቡራኬ መንፈሳዊ አገልግሎት ይሰጣሉ፤ 6ኛው ፓትርያርክ ብፁዕ ወቅዱ አቡነ ማትያስ ደግሞ፣ የአስተዳደሩን (የቢሮውን) ሥራ እያከናወኑ አጠቃላይ አመራር ይሰጣሉ፡፡
ቤተ ክርስቲያኒቱ ለሁለቱም ፓትርያርኮች እኩል የአባትነት ክብር የምትሰጥ ሲሆን፤ አገልግሎቷን በምታከናውንባቸው የዓለም ክፍሎች ሁሉ የሁለቱንም ስም በቅደም ተከተል ትጠራለች፡፡
በሁለቱም ሲኖዶሶች በኩል ቀኖናዊ ጥሰት እንደተፈጸመና ሁለተኛው ፓትርያርክ ሰማዕተ ጽድቅ አቡነ ቴዎፍሎስ ለሞት ተላልፈው ከተሰጡበት ጊዜ ጀምሮ መሰል ስሕተቶች በተደጋጋሚ መታየታቸውን መግለጫው አውስቷል፡፡ ይህም፣ ቅዱስ ሲኖዶስ ከጊዜው ጋራ አብሮ ለመሔድ በሚል የቤተ ክርስቲያኒቱን መብት የማስጠበቅ ሓላፊነቱን ባለመወጣቱ የተከሠተ እንደሆነ አስረድቷል፡፡ ጥፋቱና የዓመታት ልዩነቱ የምእመናኑን ልብ በሐዘን እንደሰበረው ጠቅሶ፣ ያለፉትንም ኾነ በሕይወት ያሉትን በጋራ ይቅርታ ለመጠየቅ ልኡካኑ በጋራ መወሰናቸውን አስታውቋል፡፡ ከሁለቱ ሲኖዶስ መዋሐድ በኋላ ቤተ ክርስቲያኒቱን ከዳግም ክፍፍል ለመጠበቅና ሉዓላዊነቷን ለማስከበር ቅዱስ ሲኖዶሱ ሕጉንና ሥርዐቱን ያገናዘበ ደንብ እንዲወጣ ልኡካኑ መስማማታቸውን ጠቁሟል፡፡
ከሁለቱም በኩል የተላለፈው ቃለ ውግዘት፣በአንድነት በሚካሔደው የቅዱስ ሲኖዶስ ምልዓተ ጉባኤ እንዲፈታ በሰላም ልኡካኑ በአንድ ድምፅ የወሰነ ሲሆን፣ ከልዩነቱ በፊት የተሾሙ ነባር ሊቃነ ጳጳሳት፣ ስማቸውና ክብራቸው ተጠብቆ በውጭ ሀገርም ኾነ በሀገር ቤት እንዲመደቡና እንዲያገለግሉ፤ ከልዩነቱ በኋላ የተሾሙት ኤጲስ ቆጶሳት፣ ጳጳሳትና ሊቃነ ጳጳሳት ደግሞ ስማቸውን እንደያዙ ቅዱስ ሲኖዶስ እንዲቀበላቸው፣ በውጭም ኾነ በሀገር ቤት አህጉረ ስብከት ተመድበው እንዲያገለግሉ ልኡካኑ ተስማምተዋል። የስም ተመሳስሎ ያላቸው አባቶች፣ እንደቅደም ተከተላቸው ቀዳማይ፣ ካልዓይ፣ ሣልሳይ…ወዘተ በሚል እንዲለዩ ተወስኗል፡፡
ለዕርቅ ሰላሙ ከአዲስ አበባ የተወከሉት ልኡካንና የአስተባባሪው ኮሚቴ አባላት ሰሞኑን የሚመለሱ ሲሆን፤ ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ መርቆሬዎስና አብረዋቸው ያሉት አባቶች፣ ምእመናኑን ተሰናብተው ከነሐሴ አጋማሽ በኋላ እንደሚመለሱ ተጠቁሟል፡፡ በጠቅላይ ቤተ ክህነቱ ምክትል ሥራ አስኪያጅ የሚመራና በዘጠኝ ንኡሳን ክፍሎች የተዋቀረ የአቀባበል ዐቢይ ኮሚቴ መቋቋሙ ታውቋል፡፡
በይፋዊ መግለጫው ላይ የተገኙት ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ፣ለዕርቀ ሰላሙ በተደጋጋሚ የተደረጉ ጥረቶች ሳይሳኩ ሲኖዶሳዊ አንድነቱ መዘግየቱን፣መንግሥትም የድርሻውን አለመወጣቱን ጠቅሰው ይቅርታ ጠይቀዋል። “ዋነኛው የጥላቻ ምሶሶ በይፋ ተናደ” በማለት ስምምነቱን ያሞገሱት ዶ/ር ዐቢይ፣ የሁላችን ኩራት የሆነችው ቅድስት ቤተ ክርስቲያን ከሁለት መከፈሏ ብቻ ሳይሆን በሁለቱም ወገን ውግዘትና ነቀፋ ሲዘራ አያገባኝም ብሎ የቆመ ኃይል ሁሉ ዛሬ ሊጸጸት ይገባዋል፤ ሲሉ ወቅሰዋል። አንድነቱ ቀድሞ ቢመለስ ኖሮ የኢትዮ ኤርትራ ችግር አይዘገይም ነበር ያሉት ጠቅላይ ሚኒስትሩ፣ አንድነቱ ከተመለሰ ዘንድ ደግሞ ቤተ ክርስቲያኒቱ የውስጥ ችግሮቿን በራሷ ከመፍታት በሻገር ለሀገር ለላምና ልማት የመጸለይ፣ የመገሠጽና የማስታረቅ ተግባሯን እንድትፈጽም አሳስበዋል፡፡
የአንድነቱን መመለስ በሀገር ቤት ለማብሠር ብዙ ሺሕ ምእመናን በተገኙበት በሚሌኒየም አዳራሽና በተለያዩ ከተሞች የዕውቅናና የምስጋና መርሐ ግብር እንደሚደረግም ዶ/ር ዐቢይ አስታውቀዋል፡፡