Administrator

Administrator

“ምስጋናዬና ፍቅሬ ከልብ ነው”
ከአራት ዓመታት በኋላ በኢትዮጵያ ውስጥ የመጀመሪያው የሆነው የሙዚቃ ድግሴ እጅግ ባመረ መልኩ ተጠናቋል። የባህርዳር ህዝብ ወደ ከተማዋ ስገባ ካደረጉልኝ አቀባበል ጀምሮ፣ በቆይታዬ ወቅት ባሳዩኝ ፍቅርና ክብር እንዲሁም መስተንግዶ ልቤ ተነክቷል - እወዳችኋለሁ! የዝግጅቱ ዕለት ስቴዲየም ተገኝታችሁ የታደማችሁ በሙሉ በተለይም ደግሞ ከሩቅ አካባቢዎች፣ ከአራቱም ማዕዘን መጥታችሁ ኮንሰርቱን ለተካፈላችሁ ሁሉ ምስጋናዬና ፍቅሬ ከልብ ነው።
የሙዚቃ ስራዎቼን ማቅረብ ከጀመርኩ ጊዜ አንስቶ፣ መላው የኢትዮጵያ ህዝብ የማይገባኝን ሁሉ እንዳደረገልኝ በድጋሚ በመመስከር፣ ሁሌም በፍፁም ታማኝነት፣ እናንተን እንደማገለግል ሳረጋግጥ በታላቅ ኩራት ነው።
እግዜር ያክብርልኝ!
አመሰግናለሁ ባህር ዳር!
አመሰግናለሁ ኢትዮጵያ!
(ከቴዲ አፍሮ ፌስቡክ)
 እጅግ ከብዙ ተደጋጋሚ ሙከራዎች በኋላ በማስታወቂያ ብቻ ተገድቦ ያልቀረው፤ “ኢትዮጵያ ወደ ፍቅር” የተሰኘው የብላቴናው የሙዚቃ ኮንሰርት፣ እውን ሆኖ፣ በስኬት ተጀምሮ በስኬት ተጠናቋል። የኮንሰርቱ አዘጋጆች /በተለይም ቴዲ አፍሮ/ ከሙዚቃ ኮንሰርቱ አንድ ቀን ቀደም ሲል፣ በወልድያ ከተማ በተቀሰቀሰ ተቃውሞና እሱንም ተከትሎ፣ በሞቱት ሰዎች ምክንያት ፕሮግራሙ እንዲሰረዝ ብዙ ዓላማ ከነበራቸው “አዛኝ ቅቤ አንጓቾች” በኩል የተከፈተውን ፕሮፓጋንዳ፣ እንዳላየ ለማለፍ ተገደዋል። ሁሉን እሰማለሁ ካልክ ከሁሉም አትሆንም፤ ወዳጄ።
በዛሬ ጊዜ የላፕቶፓቸውን ኪ-ቦርድ፣ ለነገርና ለቦይኮት ያቀባበሉ የዘመናችን ተዋጊዎች ዘንድ አድመኝነት እንጂ ማስተዋል ብሎ ነገር የለም። ይህን የሙዚቃ ድግስ ለማዘጋጀት አርቲስቱና ተባባሪዎቹ ብዙ ድካምና መከራ ከፍለው ባህር ዳር በተገኙበት፣ የመድረክና ተያያዥ ውድ ዝግጅቶች በተጠናቀቁበት፣ ብዙ የብላቴናው አድናቂዎች ከመላው ኢትዮጵያ ባህር ዳር በታደሙበት፣ እጅግ ብዙ ትኬቶች ተሽጠው ባለቁበት--- 11ኛው ሰዓት ላይ የአባ ምን ገዴ ልጆች፤ የራሳቸውን መደበኛ የዕለት ተዕለት ተግባራቸውን አንድም ሳያዛንፉ እየከወኑና ጠቆር ያለ ማኪያቶኣቸውን እየላፉ፣ በሚነካኩት ሞባይላቸው፣ በድፍረት የኮንሰርቱን መሰረዝ ጠይቀዋል።
ሁኔታው ወዳጄ ናቲ ማን፣ ከወር ገደማ በፊት ያጫወተኝን እንባ አስጨራሽ ገጠመኙን አስታወሰኝ። ናቲ መኪና አልባ ተከራይን ፈልጎ ማግኘት በሚቸግርበት አንድ የሸገር ኮንዶሚኒየም ብሎክ ነበር እሚኖረው። የኮንዶሚኒየሙ ግቢ ሁሌም በጊዜ፣ በተከራዮቹ መኪና ጥቅጥቅ ብሎ ይሞላል። አንድ ቀን ናቲ ወደ ግቢው ሲገባ ከፊቱ ሌላ ባለ መኪና ቆሟል። የብሎኩ ዘበኛ፣ ሰውየውን፣ የግቢው መኪና ማቆሚያ ስለሞላ መኪናውን ውጭ እንዲያሳድራት በማመናጨቅ እጁን እያወናጨፈ ነገረው። ይሄኔ ሰውየው መስኮቱን ዝቅ አድርጎ፣ ዘበኛውን በመጥራት እንዲህ አለው፡-
“እንደው የአስር ብር ኮንጎ ጫማህን ውጭ እማታሳድር ሰውዬ፣ አፍህን ሞልተህ የሚሊዮን ብር መኪናን ውጭ አሳድር ስትል አይቀፍህም?”
መቼም ምን ለማለት እንደፈለግሁ፣ ይገባችኋል ብዬ ተስፋ አደርጋለሁ፡፡ የሆነው ሆኖ፣ ቴዲ አፍሮ እጅግ በበዛ መሬት አንቀጥቃጭ የህዝብ ፍቅር ታጅቦ ድግሱን ከውኗል። ድግሱም፤ “Bahir Dar, are you ready?!” ከሚለው ከብዙ ናፍቆት በኋላ ከተሰማው የብላቴናው ድምፅ፣ ሶስት አራት ሰዓት ቀድሞ በኢትዮጵያዊነት ቀለማት እጅግ አሸብርቆ ቆይቷል። ከፍቅርና አንድነት ግምጃ ተራቁተን ባዶ በቀረንበት በዚህ ዘመን፣ እንደ ኢትዮጵያዊ፤ የቀረን አስተሳሳሪ ምልክት፣ አንድ ግለሰብ ብቻ መሆኑን ስታይ ሆድ ይብስሃል። እንደ ኢትዮጵያዊ ማሰብ፣ እንደ ኢትዮጵያዊ መኖርና እንደ ኢትዮጵያዊ መዘመርን ለተጠሙ ወገኖች ሁሉ ግን ምሽቱ በቀላሉ እሚረሳ ሆኖ አላለፈም።
በተለይም ወደ ስታዲየሙ በተወሰኑ ወጣቶች አማካኝነት፣ የኦሮሚያ ክልል ባንዲራ ሲገባ የተሰማው የህዝብ ድጋፍና ጭፈራ ልብን አብዝቶ እሚያሞቅ ነበር። ጭብጨባና ድጋፉን ተከትሎም፤ “ኦሮሚያ! ኦሮሚያ!” የሚለው የቀመር የሱፍ ዜማ፣ በታዳሚው አንደበት በጋራ ተዚሟል። ወዲያው ከመድረኩ የአሊ ቢራ ሙዚቃ ተከፍቶ በአንድነት ተጨፍሮበታል።
እንዲህ እንዲህ እያለ የቀጠለው ኮንሰርት፣ ወደ ሁለት ሰዓት አቅራቢያ፣ ከብዙ ጥበቃ ትዕግስትና ፈተና በኋላ የተናፋቂውን “ሰው!” ድምፅ ማሰማቱ አልቀረም።
“Bahir Dar, are you ready?!”
ወዳጄ፤ ልክ እንደኔ የመሬት መንቀጥቀጥን በህይወትህ አይተህ እማታውቅ ከሆነ፣ በዚህች ሰአት በዚህች ቦታ ባለመገኘትህ ልታዝን ይገባሃል። ቃላት በማይገልፀው ጩኸት፣ ሆታ፣ ግፊያና አጀብ፤ ብላቴናው እጅግ ያሸበረቀ ደማቅ መስቀል፣ ከፊቱ ያተመ ቲ-ሸርት ለብሶ፣ “አፍሪካዬ!” እያለ ወደ መድረኩ መጣ። እዚህ ጋ ዝም ብል ነው የሚሻለው፡፡ ምክንያቱም የሆነውን፣ የተሰማውን፣ የተደረገውን --- በቃላት ልገልጸው አልችልማ። አዝናለሁ!!
ከዚህ በፊት በተለያዩ ቦታዎች የብላቴናውን የሙዚቃ ድግሶች ታድሜአለሁ። ሁሉም ጋ አርቲስቱ ከህዝቡ የሚበረከትለት ድጋፍና ፍቅር ልክ የለውም፡፡ የእሁዱ ግን ይለያል፡፡ ቴዲ፤ ወደፊትም ይሄን በመሰለ የህዝብ የፍቅር ባህር ውስጥ ሰምጦ፣ መዝፈኑን እጠራጠራለሁ። እያንዳንዱ ሙዚቃ ሲጠናቀቅ በምትገኘው ፋታ መሃል፤ ”ቴዲ አንደኛ! ቴዲ የአንድነት መንፈስ!” የሚል የአድናቂዎች ሙገሳ ይንቆረቆርለት ነበር፡፡ አርቲስቱም በመሽኮርመምና በመደነቅ፣ ለተበረከተለት የፍቅር ሙገሳ፣ ምስጋናውን ሲያቀርብ አምሽቷል። አንዴ ደግሞ፤ “ዕድሜና ጤና ለቴዲ!” እያለ ህዝቡ ሞቅ ያለ ጭፈራውን አስነካው፡፡ ቴዲም በበኩሉ፤ ”ረጅም ዕድሜ ለሁላችን!” ሲል በአጸፋው መርቋል።
የባህርዳሩ ኮንርሰት በሙዚቃ ጥራት በኩልም ሊመሰገን የሚገባው ነበር። አቡጊዳ ባንድ፤ የሳክስፎን ትራምፔትና መሲንቆ ተጫዋቾችን እንደ አዲስ ጨምሮ ተገኝቷል። ከሮቤልና አበራ በተጨማሪም ሌላ ሶስተኛ የሊድ ጊታር ተጫዋች ነበረው፡፡ ሩፋኤል ያልተገኘበት ከበሮ፣ በሁለት ወጣቶች ሲደለቅ አምሽቷል። ባንዱ የስቱዲዮን “ኢፌክት” ለማምጣት በተጠጋ ውጤታማ “አኪውሬሲ”፣ ሙዚቃውን ሲጠበብበት  አምሽቷል። ብላቴናው፤ “አፍሪካ”፣ “ግርማዊነትዎ” እና “ጥቁር ሰውን” ከበፊት አልበሞቹ ላይ እንዲሁም “ኢትዮጵያ”፣ “ሰምበሬ”፣ “ማር እስከ ጧፍ”፣ “አናኛቱ”፣  “ያምራል”፣ “ታሞልሻል”፣ “እማ ዘንድ ይደር”፣ “ቴዎድሮስ” እና “ማራኪዬ”ን ከአዲሱ አልበሙ ተጫውቷል። በተለይ “አናኛቱ፣ ሰምበሬ፣ ኢትዮጵያ፣ ማር እስከ ጧፍና ቴዎድሮስ”ን ሲጫወት፣ የህዝቡ የዝማሬና አንድነት መንፈስ ለጉድ ነበር።
/Some awkward moments:)
ኮንሰርቱ በሁለት ምዕራፍ የተከወነ ነበር። በመሃል ቴዲና ባንዱ ለእረፍት ሲወርዱና በድንገት የዲጄው የሙዚቃ ግብዣ በቴክኒክ ብልሽት ምክንያት ሲቋረጥ፣ ከፍተኛ የተቃውሞ ድምፆች ከተለያዩ የስታዲየሙ ክፍሎች መስተጋባት ጀመሩ። እንዲህ ያለውን የተቃውሞ መንፈስ፣ ብዙም የፈለጉት እማይመስሉት የአርቲስቱ የቅርብ ሰዎች፣ በተለይም ማኔጀሩ አቶ ጌታቸው፣ ወደ መድረኩ ጫፍ ወጥቶ፣ ዲጄውን ሲቆጣው ተስተውሏል። “በሙዚቃ ያዝልን” አይነት ነው፤ ነገሩ። ይህ ትዝብት ግን ከመድረኩ በቅርብ ርቀት የተገኘ ያንድ ታዳሚ አረዳድ መሆኑ ይታወቅልኝ፡፡ ያም ሆኖ፣ የተቃውሞ ድምፆችን ማየል ከመድረክ ጀርባ (ባክስቴጅ) ሆኖ የሰማው አርቲስቱ፤ በተለመደ የሃይል መልዕክቱ እዛው ሆኖ፣ ትህትናን ባጀበ ድምፅ “ፍቅር ያሸንፋል!!!” ሲል አረጋግቷል። ቴዲ ዘፋኝ ብቻ እንዳልሆነ ለመመስከር፣ እንዲህ ባሉ አስጨናቂ ገጠመኞች መሃል መገኘትን ይጠይቃል።

ነገረ ጃ ያስተሰርያል
የጃ ጣጣ ሌላ የመድረክ ላይ ድራማ አሳይቶን አልፏል። ህዝቡ ከመጀመርያው አንስቶ በእያንዳንዱ የሙዚቃ ፋታ መሃል፣ “ጃ ያስተሰርያል”ን ሲጠይቅ ነበር ያመሸው። አርቲስቱ ወደ መጨረሻ፣ ዝግጅቱን በ“ጥቁር ሰው” ሊዘጋ በሚሰናዳባት ሰዓት ላይ ግን የህዝቡ ጥያቄ አይሎ፣ ግጥሞች ከፍ ባለ ድምፅ በዜማ ይሰሙ ጀመር።
ግርማዊነታቸው ከዚህ ሰረገላ
ወደ ዋገን ወርደው ሲተኩ በሌላ...
ከዚህ በኋላ የሆነው … አስፈሪ፣ አስደንጋጭ፣ በተወሰነ መልኩም አስቂኝ ነበር።
ቴዲ ህዝቡን ጠየቀ።
“ያስተሰርያል ይዘፈንላችሁ?”
ህዝቡ ከባህር ዳር ጎንደር ድረስ በሚሰማ ሃይለኛ ድምፅ “አዎ” አለ። ብላቴናው፤ ፊቱን አዙሮ ከጊታር ተጫዋቾቹ ጋር አጭር ምክክር አድርጎ ሲያበቃ፣ ወደ ህዝቡ ዞረና፡-
“እዘፍንላችኋለሁ” አለ።
በዚህ መሃል ሁኔታውን ከዳር ሆኖ ሲመለከት የቆየውና በቁጣና ብስጭት አቅሉን የሳተው የአርቲስቱ ማናጀር መድረክ ሰብሮ ገባ። ”እናንተ ናችሁ አማክራችሁ ዝፈን ያላችሁት!?” በሚል እየተጨቃጨቀ ይመስላል፡፡ ቴዲ አፍሮም ፈገግ እያለ፣ ጭቅጭቁን እንደኛው በዝምታ ነበር የታደመው፡፡
ለሰዓታት ሰላምና ፍቅር ሰፍኖበት የዘለቀው መድረክ፤ ከመቅጽበት ዝምታና ውጥረት ሞላው፡፡ በዚህ መሃል ህዝቡ፤ “ቴዲ አይፈራም!” እያለ መጮህ ጀመረ።
ቴዲም ወደ ህዝቡ በመዞር፤
“እኔ ፈርቼ አላውቅም!” መለሰ፡፡
ሌላ ሆታ፣ ሌላ ጭፈራ። አቶ ጌታቸው ቁጣና ብስጭቱን አራግፎ ከመድረክ ወረደ። አርቲስቱም፤ ጃ የፍቅር፣ የይቅርታና የእርቅ መልዕክት መሆኑን ጠቅሶ፣ ነገር ግን ማንም እንዲከፋው ስለማይፈልግ ኮንሰርቱን በ“ጥቁር ሰው” መዝጋቱ እንደሚሻል በትህትና አስረድቶ፣ ዝግጅቱን በባልቻ ከውኖ ህዝቡን አመስግኖ፣ ከበዛ ድጋፍና ፍቅር ጋር ታጅቦ ከመድረክ ወርዷል።
(ከEil jah ፌስቡክ)


    የኦሮሚያ ክልላዊ መንግስት ከአንድ ዓመት በፊት በክልሉ የተለያዩ አካባቢዎች የተቀሰቀሰውን ብጥብጥ ተከትሎ፣ታስረው የነበሩ ከ2ሺ በላይ ዜጎችን መፍታቱን አስታወቀ፡፡ በትላንትናው ዕለት የክልሉ ፕሬዚዳንት አቶ ለማ መገርሳ በሰጡት መግለጫ፤2 ሺ 345 እስረኞች  በምህረት መፈታታቸውን የተናገሩ ሲሆን ከእነዚህ ውስጥ 1 ሺ 568 ያህሉ በፍርድ ቤት ጥፋተኛ ተብለው የተፈረደባቸው እንደነበሩ  ገልጸዋል፡፡
መንግስት አገሪቱን ለማረጋጋትና የፖለቲካ ምህዳሩን ለማስፋት፣ የፖለቲካ እስረኞች እንደሚፈቱ መግለጹን ተከትሎ፣ ባሳለፍነው ሳምንት ዶ/ር መረራ ጉዲናን ጨምሮ 500 የሚደርሱ እስረኞች የተፈቱ ሲሆን የኦሮሚያ ክልል እርምጃም የዚሁ ውሳኔ አካል እንደሆነ ታውቋል፡፡

ቀበሮ መሞቻዋ ደርሶ በዱር አራዊት ፊት ትናዘዛለች፤ አሉ፡፡
“ወዳጆቼ ሆይ! እንግዲህ እኔ ከዚህ ዓለም መሰናበቴ ነው፡፡ ስለዚህ ጥቂት ቃላት ልናገር፤ አያ አንበሶ ጉልበት ባታበዛ ጥሩ ነው፡፡ እሜት ጦጢትም ብልጣ ብልጥነቱን አታብዢው! ዝንጀሮ ወሬ እያቀባበልክ፣ የዱር አራዊቱን እርስ በርስ አታባላቸው፡፡
ከርከሮ ቀን አመቸኝ ብለህ፣ አቅመ ደካሞችን አታጥቃ፡፡
ነብር አንዴ ሰሶችን፣ አንዴ የሜዳ አህዮችን፣ አንዴ ፍየሎችን እንዳፈተተህ እያሳደድክ መብላትህን ጋብ አድርገው፡፡
ድብ ማድባትህን ተው!
ዱኩላ አመሻሹ ላይ የቤት እንስሳት ለማጥቃት መውጣትህን አቁም፡፡
ጅብ ለአህዮች ብታዝን ጥሩ ነው፡፡ ታቀብ!
ዝሆን ሳታንቀላፋ ወዳጆችህን ተግተህ ጠብቅ፡፡
ጎሽ ልጄን ለማዳን በሚል ሰበብ፣ ሌሎችን መውጋት፣ ዘዴው የተበላ ዕቁብ ስለሆነ ማንንም እንደማታታልል ዕወቅና ተቆጠብ….
በዚህ ዓይነት ስለ ሁሉም ማስረዳቷን ስትቀጥል፣ ድንገት አውሬዎቹ ሁሉ አጉረመረሙባት!
አንበሳ ከሁሉ በላይ ተቆጣ፡፡
ነብር ሊያንቃት ተቁነጠነጠ፡፡
ዝሆን መሬቱን ይጭር ገባ፡፡
ጎሽ በንዴት ዛፍ እየታከከ፣ ቀበሮን ዘሎ ሊወጋ አሰፍስፏል!
ሁሉም ሊወነጨፉባት እንደሆነ እመት ቀበሮ ስለተገነዘበች፡-
“ጎበዛዝ አውሬዎች ሆይ! እንደው ለጊዜው ተንፍሰን እንሙት ብለን ነው እንጂ የተባላችሁትን እንደማትፈፅሙት‘ኮ እናውቃለን!” አለችና፣ ክልትው ብላ ወድቃ ቀረች!!
* * *
የሚፈልገውን ለማለት የሚችል፣ የታደለ ህዝብ ነው! የሚፈልገውን መመገብ የሚችል የታደለ ህዝብ ነው! የትም ቦታ በነፃነት መንቀሳቀስ የሚችል የታደለ ህዝብ ነው፡፡
“ደብዳቤ ቢፅፉት እንደቃል አይሆንም
እንገናኝና ልንገርሽ ሁሉንም”
ለማለት የሚችል የታደለ ህዝብ ነው!
የጠየቀው የሚፈፀምለት የታደለ ህዝብ በመሆኑ ያስቀናል፡፡ ያለ ደጅ-ጥናት፣ ያለ መጉላላት፣ ያለ ድህነት ህይወቱን የሚመራ ህዝብ እጅግ ያስቀናል!
በአገሩ የመጣ ማናቸውም ነገር የሚቆጨው፣ የሚያንገበግበው ምሁር ያለው ህዝብ፣ የተቀደሰ ነው! ለዕድገቱ የሚበጅ ዓይነት ትምህርት የሚማርና ሁሌ ከአትሮንሱ ግርጌ የሚገኝ ህዝብ የታደለ ነው! ይጭነው አጋሠሥ፣ ይለጉመው ፈረስ ያለው ህዝብ ማንንም ያስቀናል!
“ከአገር እኖር ብዬ
ልጅ አሳድግ ብዬ
ለባሻ ዳርኩለት ሚስቴን እቴ ብዬ!”
ሳይል፣ ሳይሳቀቅ፣ ሳይገፋ የሚኖር ህዝብ፣ አምላክ የመረቀው ህዝብ ነው!
“ለመቶ ሃምሣ ጌታ
ስታጠቅ ስፈታ
ነጠላዬ፤ አለቀ በላዬ!”
የማትል ምስኪን እናት ያለችው አገር፣ ዕድለኛ አገር ነው! ፍትሑ የተስተካከለ፣ ዲሞክራሲው ያልተበረዘ፣ አስተዳደሩ ያልተዛባ፣ ጤናው የተጠበቀ፣ ልማቱ የሚያኮራ፣ የማይዋሽና የማይዋሽበት ህዝብ፤ ተስፋው የሚለመልም፣ የተመኘው የሚፈፀምለት ህዝብ ነው! አገራችንና ህዝቧ እንዲህ ያለ ፀጋና ባለፀጋነት ትጎናፀፍ ዘንድ፤ የሁላችን ትጋትና ርብርብ፣ የሁላችን የመንፈስ ፅናት፣ የሁላችን የባህል ትሥሥር ሊኖር ይገባል!
አገርና ህዝብ የማሳደግ ጉዞ መቼም ቢሆን አጭር ሆኖ አያውቅም፡፡ አልጋ በአልጋም አይደለም! የምንከፍለው ግብር ተመጣጣኝ ጥቅምና ዕድገት እናገኝ ዘንድ ነው! የምንሄድበት መንገድ እንዲገነባልን፣ የምንገለገልበት መብራትና ውሃ እንዲኖረን፣ ልጆቻችንን የምናስተምርበት ት/ቤትና የምናሳክምበት ሆስፒታል እንዲኖረን ነው ከደሞዛችን፣ ከንግዳችን፣ ከምርታችን ቆጥበን ግብር የምንከፍለው! “እኔ ግብር ከፋይ ነኝ!” ብለን እንድንኮራ ነው ልፋታችን! በእርግጥም “አገሬ ምን ትሠራልኛለች” ማለት ብቻ ሳይሆን፣ “እኔ ለአገሬ ምን እሠራለሁ?” ማለት የሚቻለው ያኔ ነው! ለዚህ አርቆ ማስተዋል፣ አስቦ መራመድ ወሳኝ ነው! ከስሜት ይልቅ ብስለት አያሳጣን የሚባለውም ለዚህ ነው! ለስሜታዊነት፣ ለምሬት፣ ለትኩሳት፣ ለእዚህም እዚያም መነሳሳት የሚገፋፋ መመሪያዎችን፣ አዋጆችንና እርምጃዎችን በላይ በላዩ ከማከል በፊት ቆም ብሎ ማሰብን ብንለምድ መልካም ነው፡፡ በየትኛውም ወገን ያለን የሀገራችን ሰዎች ከስሜት ይልቅ ብስለት አያሳጣን ብለን የምናይበት መንገድ እንሻ!!

Saturday, 27 January 2018 11:52

‹‹…ጤናማ እናትነ ት….››

 እናት ሁሉም ነገር ነች፡፡ እናት መፍትሔ ነች፡፡ እናትነት ዘመን የማይሽረው መቼም የማይቀየር ነገር ነው፡፡ እናትነትን ምንጊዜም …ምንም አያደበዝዘውም። -
ወ/ሮ በለጥሻቸው ታደሰ
ከላይ የምትመለከቱት ፎቶግራፍ በፊስቱላ ሕመም ምክንያት ሲሰቃዩ የነበሩ ወጣት ሴት ልጆች እና ከሕመሙ ጋር ለረጅም አመታት አብረው የኖሩ አረጋዊት ሴት ታክመው በመዳናቸው የሚያሳዩት የደስታ ሳቅ ነው። የሐምሊን ፊስቱላ መስራች ዶ/ር ካትሪን ሐምሊን በታካሚዎቹ መካከል ምስላቸው ይታያል፡፡
በዚህ እትም የምናስነብባችሁ የፊስቱላ ታካሚዎች ከሆስፒታሉ ከወጡ በሁዋላ የሚያርፉበት በታጠቅ አካባቢ የሚገኘው የደስታ መንደርን የስራ እንቅስቃሴ ነው፡፡ በመንደሩ ካነጋገርናቸው ባለሙያዎች መካከል ወ/ሮ በለጥሻቸው ታደሰ  የድርጅቱ ስራ አስኪያጅ ይገኙበታል። ወ/ሮ በለጥሻቸው የደስታ መንደር ምን ስራ እንደሚሰራ አብራርተዋል፡፡አንዲት ታካሚ የነገረችንን ታነቡ ዘንድ እነሆ፡፡
‹‹….እኔ እንደተዳርኩ ነበር በአመቱ ያረገዝኩት። ስዳር የአስራ አምት አመት ልጅ ነበርሽ ብለውኛል። ታዲያ በአመቱ ልጅ ተረገዘ፡፡ የመውለጃ ቀኔ ሲደርስ ግን ጭንቅ ሆነ፡፡ በአካባቢዬ የነበሩ የልምድ አዋላጅ እንደገናም በዘመናዊው የማዋለድ ተግባር ሰልጥነዋል ተብሎ ተጠርተው መጡ፡፡ እንግዲህ እሳቸው ተጠርተው የመጡት በሁለተኛው ቀን ነበር፡፡ እሳቸውም አይተው …አ.አ.ይ ቀላል አይመስለ ኝም፡፡ ነገር ግን ልሞክር ብለው አንድ ቀን አደርኩ፡፡ ከዚያ በሁዋላ ቅርብ ወደሆነው ጤና ጣብያ በሸክም በቃሬዛ ወሰዱኝ፡፡ ታዲያ የተረገዘው ልጅ ሞቶ እኔም እንዳልሆን ሆኜ ተገላገልኩ፡፡ ከዚያ በሁዋላ ግን ወደቤቴ ተመልሼ ሳለሁ ዝም ብሎ ልብሴ ይበሰብሳል። ሽንትም አይይዘኝም፡፡ የሚበላ የሚጠጣ ሲሰጡኝ ታዲያ ሽንቴ እየበዛ እንዲያውም እየሸተተ አስቸገረ፡፡ እኔም ለሁለት ወር ከተሰቃየሁ በሁዋላ በቃኝ አልበላም አልጠጣም አልኩኝ፡፡ ለምን ቢሉኝ … የሆንኩትን ነገርኩዋቸው፡፡ የአራስነት መስሎኝ እንጂ የሚፈሰው ፈሳሽ ሽታው አስቸግሮኛል አልኩዋቸው፡፡ እንዲያው በሰው ፊት ልቁም ወይም ልቀመጥ …ብቻ ስነሳ ልብሴ በስብሶ በእግሬ ላይ ሽንት ፈስሶ ይገኛል፡፡  ባለቤቴም ወደቤተሰቦቼ ዘንድ መለሰኝ፡፡ የባህል ሕክምናው… ጸበሉ… ሁሉም አልቀረኝ። አንዱም መፍትሔ አልሆነም፡፡ ውሎ አድሮ ግን የሐምሊን ፊስቱላ ሐኪሞች ወደኛም መንደር ደርሰው ነበርና ለሕክምና አመጡኝ፡፡ በ2001/ዓ/ም እንደመጣሁ ታከምኩ፡፡ ለሁለት አመት ከሆስፒታል ከቆየሁ በሁዋላ ወደደስታ መንደር በ2003/ዓ/ም ተዛወርኩ፡፡ አሁን በካፌው ስራ ሰልጥኜ እየሰራሁ እገኛለሁ፡፡ ወደአገሬም እንዳልመለስ ከሕክምናው መራቅ አልችልም፡፡ አሁን ግን ቤት ተከራይቼ ስራዬን እየሰራሁ ይኼው እኖራለሁ። እግዚአብሔር ይመስገን ሽንቴንም በላስቲክ ከረጢት አድርገውልኝ ከሰው ጋር እውላለሁ፡፡…››
የታካሚ ምስክርነት
ደስታ መንደር ማለት በፊስቱላ የተጎዱ ወገኖች ዘለቄታዊ  የሆነ እገዛ የሚያገኙበት …እራሳቸውን ችለው የሚኖሩበትን ሙያ የሚቀስሙበት …ከህብረተሰቡ ጋር ተመልሰው ለመቀላቀል የሚያስችላቸውን የተለያየ የእደጥበብ ትምህርት የሚማሩበት ተቋም ነው፡፡ ይህ ቦታ በመንግስት ስር ይተዳደር የነበረ ሌላ ተቋም የነበረ ሲሆን በሁዋላ ግን ለዶ/ር ካትሪን ሐምሊንና ለሆስፒታሉ በተለይም የፊስቱላ ሕመማቸው በቀላሉ ለማይድንላቸው ሴቶች የተሰጠበት አላማ ከፊስቱላው ጋር ሲኖሩ በምን ሁኔታ እራሳቸውን ደግፈው መኖር አለባቸው ለሚለው ነበር፡፡ አሁን ግን የታካሚዎቹ ቁጥር እየጨመረ በመሄዱ እና በዘላቂነት ለማኖር ከፍተኛ በጀት በማስፈለጉ ምክንያት በዘላቂነት ማኖር አልተቻለም፡፡ ከዚህም በተጨማሪ በማህበራዊውም አቅጣጫ ከተለያዩ አካባቢዎች የመጡት ታካሚዎች ወደየመጡበት ህብረተሰብ ቢመለሱ የበለጠ ሊጠቀሙ እንዲሁም ሞራላቸው ሊታደስ ይችላል የሚል እምነት ስላለ አስፈላጊው ሕክምና ከተደረገላቸው እና ለመቋቋም የሚያስችላቸው በቂ እውቀት ካገኙ ወደመጡበት አካባቢ በመውሰድ ማቋቋም ይሻላል ወደሚለው ዝንባሌ መሄድ ግድ ሆኖአል፡፡ ስለዚህም ደስታ መንደር ጠንከር ያሉት ታካሚዎች እየተመረጡ ወደሀገራቸው በመሄድ ጤናቸውን ጠብቀው የራሳቸውን ስራ እየሰሩ እንዲኖሩ የሚበቁበት ማእከል ሆኖአል፡፡  ደስታ መንደር የተባለበትም ምክንያት በቆይታቸው ወቅት እስኪያገግሙ ድረስ ደስ እያላቸው ስለሚታከሙ ነው፡፡
ወ/ሮ በለጥሻቸው በመቀጠል እንደገለጹት ከ100 %ታካሚዎች መካከል 4% እና 5 % የሚሆኑትን ታካሚዎች በቀዶ ሕክምና ምንም እንከን ሳይወጣለት ለማዳን እንደማይቻል ሐኪሞች ይመሰክራሉ፡፡ ስለዚህም  ወደመንደሩ የሚላኩት የፊስቱላ ታካሚዎች ከ2-3 ወር ወይንም እስከ አመት ድረስ ሊሆን በሚችል ጊዜ ከፍ ያለ የህክምና ስራ የሚደረግላቸው እና እንዲሁም ከቤተሰቦቻቸውም ሆነ ከራሳቸው ጋር በመመካከር በዘላቂነት ሽንትን በውጭ ሰውነታቸው በኩል ከልብሳቸው ስር በሚንጠለጠል የላስቲክ ከረጢት  እየተቀበሉ በዘላቂነት እንዲኖሩ የሚመቻችላቸው ናቸው፡፡  ስለዚህም እነዚህ ሴቶች በተፈጥ ሮአዊው መንገድ ሽንታቸውን ማስወገድ የማይችሉ ሲሆን በሚሰጣቸው የላስቲክ  ከረጢት ግን እየተ ቀበሉ በሚኖሩበት ጊዜ ከአሁን ቀደም በሕመም በነበሩበት ጊዜ የነበረው ከማህበረሰቡ መገለል እንዲሁም የጤና እውክታ እና ማህበራዊ ጫና በማይደርስባቸው ሁኔታ እራሳቸውን በመቆጣጠር እና በአቅራቢያ ቸው በሚገኝ የጤና ተቋም የህክምና ክትትላቸውን በማድረግ በጥሩ ሁኔታ ሕይወታቸው እንዲቀጥል አስፈላጊው ሁሉ ይደረጋል፡፡ ከእነዚህ ሴቶች መካከል ድጋሚ ትዳር የሚመሰርቱም አሉ፡፡ በእርግጥ ሽንትን ለማስወገድ የሚጠቀሙበት የላስቲክ ከረጢት የሚመጣው ከውጭ ሀገር ሲሆን እስከአሁን የሚሰጣቸው ግን ከሆስፒታሉ ነው፡፡ አጠቃቀሙም አንዱ ከረጢት ምናልባት ለሶስት ወይም አራት ጊዜ ያህል ሲሆን ከዚያ ባለፈ የሚጣል ነው፡፡ ታካሚዎች በዚህ ሁኔታ የወደፊት ሕይወታቸውን እንዲቀጥሉ ለማድረግ በቅድሚያ አስፈላጊው የምክር አገልግሎት ተሰጥቶአቸው ተስማምተው እንዲወስኑ ይደረጋል፡፡
ከዚህ ውሳኔና የቀዶ ሕክምና በሁዋላ ግን ለሶስት ወር በደስታ መንደር ተቀምጠው በቅርብ የህክምና ክትትል እያደረጉ በምን ሁኔታ መገልገል እንዳለባቸው ትምህርት ይሰጣቸዋል፡፡ ከዚህ በተጨማሪ ደግሞ የተለያዩ ለኑሮ የሚያግዙ ትምህርቶችን እንዲወስዱ ይደረጋል። በደስታ መንደር ቆይታቸው በጤና በተመሳሳይም ወደፊት እራሳቸውን በምን መንገድ ችለው ወደ ትውልድ መንደራቸው ቀረብ ብለው መኖር ይችላሉ የሚለውን በጥናት በመመስረት ተግባራዊ በመደረግ ላይ ይገኛል። ሀሳቡ የሚጀምረው ከእነሱ ጋር በመመካከር ሲሆን በአካባቢያቸው ምን ቢሰሩ ያዋጣቸዋል? የሚለው ከግንዛቤ ይገባል፡፡ አነስተኛ ቢሆንም ለስራ መነሻ የሚሆናቸው ገንዘብም ይሰጣቸዋል፡፡
አቶ ጉቱ ሰቦቃ በደስታ መንደር ለሶስት ወር ያህል ከቆዩ በሁዋላ ወደየመንደራቸው ወይንም አካባ ቢያቸው የሚሄዱ ታካሚዎች ከሄዱ በሁዋላ ያለው የኑሮ ሁኔታቸው ምን ይመስላል የሚለውን ክትትል እና ድጋፍ የሚያደርጉ ባለሙያ ናቸው፡፡ እሳቸው እንደሚሉት ሕመሙ በዚህ አካባቢ ተብሎ የማይወሰን በሁሉም ክልል የሚፈጠር እንደመሆኑ ታካሚዎች ወደመንደራቸው የሚሰማሩትም በሁሉም የኢትዮጵያ ክልል ነው፡፡ ስለዚህም ወደመጡበት ማህበረሰብ ተመልሰው ኑሮአቸውን እንዲጀምሩ …ተቋርጦ የነበረውን ሕይወት እንዲቀጥሉ ይደረጋል፡፡ ሕመሙ ሲገጥማቸው ትዳራቸው የመፍረስ… ንብረታቸው የመበተን አደጋ የሚደርስበት በህብረተሰቡ ዘንድ መገለል እና የማህበራዊ ውም ሆነ ኢኮኖሚያዊው ኑሮአቸው ስለሚ ቋረጥ ይህ ድርጅት ወደአካባቢያቸው ሲመልሳቸው እነዚህ ነገሮች መቶ በመቶም እንኩዋን ባይሆን በተቻለ መጠን ሴቶቹ እራሳቸውን የሚያስተዳድሩበትን መንገድ በመፈለግ እንዲቋቋሙ በማድረግ ነው፡፡ ይህ ስራ የሚሰራው ከባለድርሻ አካላት ጋር ነው፡፡ ስራ መስሪያ ቦታ ማግኘት አለባቸው፡፡ የገበያ ትስስር እንፈጥራለን የሚል ቃል ኪዳን ስናገኝ ገንዘብ እንዲደርሳቸው ይደረጋል፡፡ እነዚህ ነገሮች የሚሰሩት ከሴቶች ጉዳይ ቢሮ… ከሀይማኖት ተቋማት … በቅርብ ከሚገኙ መንግስታዊና መንግስታዊ ካልሆኑ ድርጅቶች እንዲሁም ለጉዳዩ ቅርብ ከሆኑ ግለሰቦች ጋር በትብብር እንሰራለን፡፡ እነዚህ ሴቶች ተቋቁመው ስራ ከጀመሩ በሁዋላ በተወሰኑ ጊዜያት ከቤታቸው ድረስ እየሄድን እውነት በአይን የሚታይ ነገር አለ ወይ ? ተግባሩ ከምን ደርሶአል? የሚለውን ክትትል እናደርጋለን፡፡
ወ/ሮ በለጥሻቸው ታደሰ የደስታ መንደር ስራ አስኪያጅ በስተመጨረሻው የገለጹት አንዲት ሴት ልጅ ተድራ ልጅ ለመውለድ ስትደርስ ጀምሮ ያለው ጥንቃቄ በአካባቢው የሚኖር ሰው ሁሉ ኃላፊነት መሆ ኑን ነው፡፡ የትዳር ጉዋደኛ …ቤተሰብ እንዲሁም የመንደር …አካባቢው ሰው ሁሉ ስለዚያች ልጅ መጨ ነቅ አለበት፡፡ ችላ ማለት አይቻልም፡፡ ምክንያቱም አንዲት እናት ደህና ሆነች ማለት ሰፈር ጎረቤቱ… ቤተሰቡ… ዘመድ አዝማዱ ሁሉ ደህና ነው ማለት ስለሆነ ነው፡፡
እናትነት ዘመን የማይሽረው መቼም የማይቀየር ውድ ነገር ነው፡፡ እናትነትን ምንጊዜም …ምንም አያደበዝዘውም፡፡


               “ትራምፕ የልቡን ስለሚናገር እወደዋለሁ” - የኡጋንዳው መሪ ዮሪ ሙሴቬኒ

   የአፍሪካ ህብረት ሊቀመንበር ሙሳ ፋኪ ናህማት፣ ፕሬዚዳንት ዶናልድ ትራምፕ በቅርቡ በአፍሪካውያን ላይ አስጸያፊ ንግግር ማድረጋቸው አግባብነት የሌለውና የአገራቱ መሪዎች በጋራ የሚያወግዙት ነው ቢሉም፣ የኡጋንዳው መሪ ዮሪ ሙሴቬኒ በአንጻሩ፣”ትራምፕ ምን ይሉኝ ሳይል የልቡን ስለሚናገር እወደዋለሁ፤ አደንቀዋለሁ” በማለት በዘለፋው አለመቀየማቸውን ገልጸዋል፡፡
ትራምፕ በቅርቡ አፍሪካውያንንና ሃይቲያውያንን በሚመለከት አስጸያፊ ንግግር ማድረጋቸው በተመድ ሳይቀር መነቀፉን ያስታወሰው ኒውስ 24፤ የህብረቱ ሊቀመንበርም ከትናንት በስቲያ ከአዲስ አበባ በሰጡት መግለጫ፣ ዘለፋው አፍሪካውያንን ያስከፋና የጥላቻ ንግግር ነው፤ ህብረቱም አጥብቆ ያወግዘዋል ያሉ ሲሆን  ህብረቱ በማካሄድ ላይ ያለውን ጉባኤ ሲያጠናቅቅ በጉዳዩ ላይ ይፋዊ መግለጫ ይሰጣል ተብሎ እንደሚጠበቅም ተናግረዋል፡፡
የኡጋንዳው መሪ ዮሪ ሙሴቬኒ በበኩላቸው፣ ትራምፕ አፍሪካውያንን በተመለከተ ያለውን አመለካከትና ስሜት ሳይሸፋፍን እቅጩን ስለሚናገር እወደዋለሁ፤ እኛ አፍሪካውያን ያለብንን ድክመት ለመናገር ቃላት አይመርጥም፣ አካፋን አካፋ ይላል በማለት በትራምፕ ንግግር አለመቀየማቸውን ገልጸዋል ብሏል ዘገባው፡፡

ለ90ኛ ጊዜ የሚካሄደው የ2018 የኦስካር ሽልማት ዕጩዎች ዝርዝር ከሰሞኑ ይፋ የተደረገ ሲሆን፣ 13 ጊዜ ለሽልማት የታጨው ዘ ሼፕ ኦፍ ዋተር፣ በአመቱ በብዛት በመታጨት ቀዳሚነቱን የያዘ ፊልም ሆኗል፡፡
የሮማንቲክ ሳይንስ ፊክሽን ዘውግ ያለው ዘ ሼፕ ኦፍ ዋተር፣ በዘንድሮው የኦስካር ሽልማት በብዛት በመታጨት ታሪክ ቢሰራም፣ በኦስካር ታሪክ 14 ጊዜ በመታጨት ክብረወሰኑን ከያዙት ታይታኒክ፣ ኦል አባውት ኢቭ እና ላላ ላንድ ተርታ በመሰለፍ ሌላ ታሪክ መስራቱ ለጥቂት ሳይሳካለት ቀርቷል፡፡
በ24 የተለያዩ ዘርፎች ዕጩዎች በቀረቡበት በዘንድሮው ኦስካር፣ በብዛት በመታጨት የሚመራው በስምንት ዘርፎች የታጨው ዳንኪርክ ሲሆን፣ ስሪ ቢልቦርድስ አውትሳይድ ኢቢንግ ሚሱሪ በ7፣ ፋንተም ትሬድ በ6 ይከተላሉ፡፡ የ22 አመቱ የፊልም ተዋናይ ቲሞቲ ቻላሜት፣ በኦስካር ታሪክ በለጋ እድሜው ለምርጥ ወንድ ተዋናይነት በመታጨት የሶስተኛነት ደረጃን መያዙን ያስታወቀው ተቋሙ፣ ሁለቱን ደረጃዎች የያዙት ጃኪ ኩፐር የተባለው የ9 አመት ታዳጊና ሚኪ ሩኒ የተባለው የ19 ወጣት መሆናቸውን አስታውሷል፡፡
ኦል ዘ መኒ ኢን ዘወርልድ በሚለው ፊልሙ በምርጥ ረዳት ተዋናይ ዘርፍ ለሽልማት የታጨው የ88 አመቱ የፊልም ተዋናይ ክሪስቶፈር ፕላመር፣ ረጅም እድሜ የገፋ የኦስካር ዕጩ በመሆን በታሪክ ተመዝግቧል፡፡
በብዛት በታጨው ዘ ሼፕ ኦፍ ዋተር ላይ የምትተውነው ኦክታቪያ ስፔንሰር፣ ለሶስት ጊዜ ለኦስካር ሽልማት በመታጨት ቀዳሚዋ ጥቁር ሴት ተዋናይት የሚለውን ማዕረግ ከቪዮላ ዳቪስ ጋር ተጋርታለች፡፡ ዴንዘል ዋሽንግተን በበኩሉ፤ ስምንት ጊዜ በመታጨት ቀዳሚው ጥቁር የፊልም ተዋናይ በመሆን ታሪክ ሰርቷል፡፡ ሁለቱም ጥቁር ተዋንያን በብዛት በመታጨት ብቻ ሳይሆን፣ በተከታታይ አመታት ለዕጩነት በመቅረብም ታሪክ መስረታቸው ተነግሯል፡፡የዘንድሮው የኦስካር ሽልማት አሸናፊዎች የሽልማት አሰጣጥ ስነ-ስርዓት፣ በመጋቢት ወር መጀመሪያ ላይ በደማቅ ሁኔታ ይከናወናል ተብሎ ይጠበቃል፡፡

   የተጣራ ሃብታቸው 113.5 ቢሊዮን ዶላር ደርሷል
   የታዋቂው አማዞን ኩባንያ መስራችና ዋና ስራ አስፈጻሚ አሜሪካዊው ቢሊየነር ጄፍ ቤዞስ ሃብት፣ ባለፈው ማክሰኞ ብቻ በ2.8 ቢሊዮን ዶላር መጨመሩን ተከትሎ፣ ግለሰቡ በአለማችን ታሪክ እጅግ ከፍተኛውን የሃብት መጠን ያካበቱ ቁጥር አንድ ባለጸጋ መሆናቸውን ፎርብስ መጽሄት ዘግቧል፡፡
ጄፍ ቤዞስ፤ አማዞን ጎ የተባለውን አዲስ ቅርንጫፍ በሲያትል ባለፈው ማክሰኞ መክፈታቸውን ተከትሎ፣ የኩባንያቸው የአክስዮን ድርሻ መጠን በ2.5 በመቶ ማደጉን የጠቆመው ዘገባው፣ በዚህም የግለሰቡ የሃብት መጠን በ2.8 ቢሊዮን ዶላር በመጨመር 113.5 ቢሊዮን ዶላር መድረሱን አመልክቷል፡፡
ከአማዞን በተጨማሪ የዋሽንግተን ፖስት ጋዜጣ ባለቤት የሆኑት ባለሃብቱ፤ በአሁኑ ሰዓት ያካበቱት የ113.5 ቢሊዮን ዶላር የተጣራ ሃብት መጠን በታሪክ ከፍተኛው ሆኖ መመዝገቡን የጠቆመው ዘገባው፣ ቢል ጌትስ በ92.5 ቢሊዮን ዶላር፣ ዋረን በፌት በ92.3 ቢሊዮን ዶላር የሁለተኛና ሶስተኛ ደረጃ ይዘው እንደሚከተሉ ገልጧል፡፡
ከኩባዊ ስደተኛ አባትና ከአሜሪካዊት እናት የተወለዱት ጄፍ ቤዞስ፣ በርካታ ኩባንያዎችን በመክፈት ትርፋማ ቢዝነስ ላይ መሰማራታቸውንና ከአጠቃላዩ ሃብታቸው 16 በመቶ የሚሆነውን ድርሻ የሚይዘው በቴክኖሎጂ የታገዘ የሽያጭ ስራ በሚያከናውነው አማዞን ኩባንያ መሆኑን የጠቆመው ዘገባው፣ ባለሃብቱ በበጎ አድራጎት ስራ ላይ በስፋት እንደተሰማሩና በቅርቡም ለሁለተኛ ደረጃ ተማሪዎች መርጃ የሚውል የ33 ሚሊዮን ዶላር የገንዘብ ልገሳ ማድረጋቸውን አስታውሷል፡፡


“ኦፕራ ከኔ ጋር ልትፎካከር? አታደርገውም! የምታደርገው ከሆነ ግን፣ ግጥም አድርጌ ነው የማሸንፋት!” - ዶናልድ ትራምፕ

    በቅርቡ በተካሄደው የጎልደን ግሎብ ሽልማት ስነስርዓት ላይ ፖለቲካዊ ይዘት ያለው ንግግር ማድረጓን ተከትሎ፣ በመጪው የአሜሪካ ፕሬዚዳንታዊ ምርጫ ዲሞክራቶችን በመወከል ከትራምፕ ጋር ትፎካከራለች ተብሎ በስፋት ሲነገርላት የሰነበተቺው ታዋቂዋ የቶክ ሾው አቅራቢ ኦፕራ ዊንፍሬይ፣ በፕሬዚዳንትነት የመወዳደር ፍላጎት እንደሌላት በይፋ ማስታወቋን ቢቢሲ ዘግቧል፡፡
ብዙዎች ለፕሬዚዳንትነት እንደምትወዳደር ሲዘግቡ ሰንብተዋል፤ እኔ ግን የምችለውንና የማልችለውን ነገር ጠንቅቄ የማውቅ ሰው ነኝ! የአሜሪካ ፕሬዚዳንት የመሆን ፍላጎት የለኝም ስትል፣ ኢንስታይል ከተባለው መጽሄት ጋር ከሰሞኑ ባደረገቺው ቃለ መጠይቅ ኦፕራ አቋሟን መግለጧን  ዘገባው አመልክቷል፡፡
ኦፕራ በ2020 በሚካሄደው የአሜሪካ ፕሬዚዳንታዊ ምርጫ እንደምትሳተፍ የሚገልጸው ወሬ በተለያዩ መገናኛ ብዙሃንና በማህበራዊ ድረገጾች በስፋት መሰራጨቱን ተከትሎ፣ በጉዳዩ ላይ አስተያየታቸውን እንዲሰጡ የተጠየቁት ፕሬዚዳንት ትራምፕ፣ “ይህ እጅግ አስቂኝ ነገር ነው፤ ኦፕራ ከኔ ጋር ልትፎካከር? አታደርገውም! የምታደርገው ከሆነ ግን፣ ግጥም አድርጌ ነው የማሸንፋት!” ሲሉ ምላሽ መስጠታቸውንም ዘገባው አስታውሷል፡፡

 ቻይና ቴሲጁ ሲቪል ኢንጂነሪንግ ግሩፕ የተሰኘው የቻይና የግንባታ ተቋራጭ ኩባንያ፣ ፉጂያን በተባለው የአገሪቱ ደቡባዊ አውራጃ የሚገኘውን የአንድ ግዙፍ የባቡር ጣቢያ ግንባታ ፕሮጀክት፣በ9 ሰዓታት ውስጥ ሙሉ ለሙሉ አጠናቅቆ ማስረከቡን ዴይሊ ሜይል ዘግቧል፡፡
ናንሎንግ በተባለው ግዙፍ የባቡር ጣቢያ ፕሮጀክት የግንባታ ስራ ላይ 1 ሺህ 500 ቻይናውያን የግንባታ ሰራተኞች መሳተፋቸውንና ይህንን ግዙፍ ፕሮጀክት በ9 ሰዓታት ጊዜ ውስጥ ለማጠናቀቅ የተቻለው የተጠናና የተቀናጀ ስራ በማከናወናቸው መሆኑን ዘገባው አመልክቷል፡፡
ሰራተኞቹ በሰባት ቡድኖች ተከፋፍለው እንዲሰሩ የተደረገ ሲሆን፣ በአንድ ጊዜ የተለያዩ ስራዎችን ማከናወን የሚያስችላቸውን ስልጠና አግኝተው ወደ ስራ መግባታቸውም ይህንን ግዙፍ ፕሮጀክት በዚህ የሚገርም ፍጥነት እንዲያጠናቅቁ እንዳስቻላቸው ተነግሯል፡፡
ባለፈው አርብ በተከናወነው በዚህ እጅግ ፈጣን የግንባታ ስራ፣ ሰባት ባቡሮችንና 23 የቁፋሮ ማሽኖችን ጨምሮ የተለያዩ የግንባታ መሳሪያዎችን መጠቀሙን የጠቆመው ኩባንያው፣ በግንባታው ሶስት የባቡር ሃዲዶችን ወደ አንድ የማቀላቀል፣ የትራፊክ መብራቶችን የመግጠም፣ የተለያዩ የእንቅስቃሴ መቆጣጠሪያ መሳሪያዎችን የመትከልና ሌሎች ስራዎች በሚገርም ፍጥነትና ጥራት መጠናቀቃቸውንም አመልክቷል፡፡


  ታዋቂው የአሜሪካ ኩባንያ ማይክሮሶፍት፣ ቶምሰን ሮይተርስ ባለፈው ረቡዕ ይፋ ባደረገው የዓመቱ የአለማችን ምርጥ 100 ታላላቅ የቴክኖሎጂ ኩባንያዎች ዝርዝር ውስጥ በአንደኛ ደረጃ ላይ በመሪነት መቀመጡን አስታውቋል፡፡
ተቋሙ የቴክኖሎጂ ኩባንያዎችን ትርፋማነትና ተቋማዊ ብቃት በመመዘን በየዓመቱ ይፋ በሚያደርገውና ሰሞኑን ይፋ ባደረገው የዘንድሮው ዝርዝር ውስጥ፣ የኮምፒውተር መሳሪያዎችን በማምረት የሚታወቀው ኢንቴል የሁለተኛነት ደረጃን ሲይዝ፣ የኔትወርክ መሳሪያዎች አምራቹ ሲስኮ ሲስተምስ ኩባንያ ሶስተኛ ደረጃ ላይ ተቀምጧል። በዘንድሮው ዝርዝር ውስጥ ከማይክሮሶፍት፣ ኢንቴልና ሲስኮ በተጨማሪ የአሜሪካዎቹ አፕል፣ አልፋቤት፣ ኢንተርናሽናል ቢዝነስ ማሺንስ ኮርፖሬሽንና ቴክሳስ ኢንስትሩመንት እስከ አስረኛ ባለው ደረጃ ላይ ተቀምጠዋል፡፡
አስከ አስረኛ ባለው ደረጃ ውስጥ የተካተቱት የሌሎች አገራት የቴክኖሎጂ ኩባንያዎች ደግሞ የታይዋኑ ሰሚኮንዳክተር ማኑፋክቸሪንግ፣ የጀርመኑ ሳፕ እና ተቀማጭነቱ በደብሊን የሆነው አክሴንቸር መሆናቸውን ተቋሙ ባወጣው መረጃ አስታውቋል።
በዘንድሮው የቶምሰን ሮይተርስ የዓለማችን ምርጥ 100 የቴክኖሎጂ ኩባንያዎች ዝርዝር ውስጥ ከተካተቱት ሌሎች ታላላቅ ኩባንያዎች መካከልም አማዞንና ፌስቡክ ይገኙበታል፡፡ ከ100ዎቹ ምርጥ የቴክኖሎጂ ኩባንያዎች መካከል 45 በመቶ ያህሉ መቀመጫቸውን በአሜሪካ፣ ጃፓንና ታይዋን  ያደረጉ መሆናቸው የጠቆመው ተቋሙ፤ ሰሜን አሜሪካ 47፣ እስያ 38፣ አውሮፓ 14 እና አውስትራሊያ 1 ኩባንያ በዝርዝሩ ውስጥ ማካተታቸውንም አመልክቷል፡፡