Administrator

Administrator

በአዲስ አበባ ከተማ  አዲሱ ገበያ ሸገር መናፈሻ አካባቢ የተገነባውና  ከ200 ሚሊዮን ብር በላይ የግንባታ ወጪ  ተደርጎበታል የተባለው  ናሁሰናይ ኢንተርናሽናል ሆቴል፤ ከነገ ወዲያ  ቅዳሜ የካቲት 23 ቀን 2016 ዓ.ም ይመረቃል።

የሆቴሉ ባለቤቶች አቶ እሱባለው ናሁሰናይና  ባለቤታቸው ወ/ሮ ሒሩት ምህረቴ እንዲሁም የሆቴሉ ዋና ሥራ አስኪያጅ አቶ መላኩ ካሳሁን በጋራ በሰጡት መግለጫ፤ ሆቴሉ  ደረጃውን የጠበቀ፣ ምቹ ስፍራ ላይ የተገነባና ለደንበኞቹ የተሟላ አገልግሎት ለመስጠት በሚያስችል መልኩ የተደራጀ መሆኑን ተናግረዋል፡፡

ሆቴሉ  46 የመኝታ ክፍሎች  ያሉት ሲሆን፤ እንግዶች ምግባቸውን እዚያው እያበሰሉ የሚመገቡበት የተሟላና የተደራጀ የገስት ሃውስ ክፍሎችንም ያካተተ ነው። አገልግሎቱንም  ከአካባቢው አንፃር ተመጣጣኝ በሆነ ዋጋ ለማቅረብ  በሚያስችል መልኩ መደራጀቱ ተጠቁሟል፡፡

የሆቴሉ ግንባታ  ሦስት ዓመታትን  እንደፈጀ የተገለፀ ሲሆን፤ ናሁሰናይ ኢንተርናሽናል ሆቴል ሙሉ በሙሉ ሥራ ሲጀምር ከ70 እስከ 100 ለሚሆኑ  ሠራተኞች የሥራ ዕድል እንደሚፈጥር ተነግሯል፡፡

ሆቴሉ  ከነገ ወዲያ ቅዳሜ  የመንግሥት የሥራ ኃላፊዎችና ጥሪ የተደረገላቸው እንግዶች በተገኙበት እንደሚመረቅ ተገልጿል።

•  የክ/ከተማው አመራሮች መርሃ ግብሩን አወድሰውታል

"ልምዴን ለወጣቱ" በሚል መሪ ቃል ዛሬ የካቲት 21 ቀን 2016 ዓ.ም ሳኦል የኩነቶች አዘጋጅና ሌጀንድ ኢንተርናሽናል ፕሮ ቴኳንዶ፣ ከልደታ ክፍለ ከተማ ወጣቶችና ስፖርት ቢሮ ጋር በመተባበር ባዘጋጁት የወጣቶች መድረክ ላይ ታዋቂው የህይወትና ስኬት አሰልጣኝና አማካሪው ዳዊት ድሪምስ ልምዱን አካፈለ።

ዳዊት ድሪምስ ከህይወት ተሞክሮውና ከንባብና ጥናቱ ልምዱን ባካፈለበት የልደታ ክፍለ ከተማ አዳራሽ፣ ወጣቶች ከአፍ እስከ ገደፉ ሞልተውት እንደነበር ተስተውሏል፡፡
   
በዛሬው መርሀ-ግብር ላይ ከዳዊት ድሪምስ ጋር ተገኝተው ልምዳቸውን እንደሚያካፍሉ ሲጠበቁ ከነበሩት ታዋቂ ግለሰቦች መካከል መንሱር ጀማል፣ ግራንድ ማስተር ሄኖክ፣ ማስተር በፍቃዱ (ኢሱ)፣ አቶ ሰኢድ፣ ዮኒ ቬጋስ እና ደራሲ መሐመድ ብርሀን ተጠቃሽ ሲሆኑ፤ በፕሮግራም መደራረብ ምክንያት መገኘት ያለመቻላቸውን ለማወቅ ተችሏል።

ለወጣቶቹ ልምድ ላከፈሉት ለዳዊት ድሪምስና ለሌሎች አካላትም ከአዘጋጆቹ ስጦታ ተበርክቶላቸዋል።

የክፍለ ከተማው አመራሮችም ዝግጅቱን ላሰናዱት ሳኦል የኩነቶች አዘጋጅ እንዲሁም ልምዳቸውን ላካፈሉት ግለሰቦች ምስጋና ያቀረቡ ሲሆን፤ እንዲህ ዓይነቱ ወጣቱን የማነቃቃት ፕሮግራም መዘጋጀቱ ወጣቱን በስነ ልቡና ለማንቃትና ለስራ ለማነሳሳት ስለሚያግዝ በየጊዜው መዘጋጀት አለበት ብለዋል፡፡

“ትልቅ ህልም አለኝ” የተሰኘ መጽሐፍ ለንባብ ያበቃው ዳዊት ድሪምስ፤ “እኔ የህይወትና ስኬት ምስጢሮች ተመራማሪ፣ አማካሪና አሰልጣኝ ነኝ” ሲል ነው ራሱን የሚገልጸው፡፡

ስለ ህልሙ ሲናገርም፤ “የኔ ትልቁ ህልም ለዘመናት የተደበቁ የህይወትና ስኬት ምስጢሮችን በጥልቀት በማጥናት፣ በመጠቀምና በማስተማር ኢትዮጵያንና አፍሪካን መቀየር ነው” ይላል፡፡

በሚሰጣቸው ተከታታይ የስኬትና የሰብአዊ ግንባታ ሥልጠናዎች የበርካቶችን ህይወት እንደቀየረ የሚነገርለት ዳዊት ድሪምስ፤ በጥረታቸውና በትጋታቸው ለድል የበቁ ስኬታማ ሰዎችን እየጋበዘ ልምዳቸውን እንዲያጋሩና ሌሎችን እንዲያነቃቁ በማድረግም ይታወቃል፡፡

ዛሬ ደግሞ እርሱ በተራው በልደታ ክፍለ ከተማ ተገኝቶ ከልምዱ በማካፈል ወጣቶችን አነቃቅቷል፡፡

ጠላቶቻችን ኢትዮጵያ ላይ የሚረባረቡት ተስፋ ስላላት ነው ያሉት ጠ/ሚኒስትር ዐቢይ አህመድ፤ ኢትዮጵያውያን ሃገራቸውን ስለሚወዱና የመጨረሻው የቁርጥ ጉዳይ ከመጣ ህይወታቸውን ገብረውም ቢሆን እንደ አባቶቻቸው አገር ስለሚያስቀጥሉ ኢትዮጵያን የማፍረስ ፕሮጀክት አይሳካም ብለዋል፡፡

ጠ/ሚኒስትሩ ይህን የተናገሩት ሰሞኑን ከሶማሌ፣ አፋር፣ ሐረሪ፣ ጋምቤላ፣ ቤኒሻንጉልጉሙዝ ክልሎችና ድሬዳዋ ከተማ አስተዳደር ተወካዮች ጋር ባደረጉት ውይይት ነው፡፡

ድሮ እኛ እንዳንገነጠል ትሰጉ ነበር፤ አሁን እኛ እየሰጋን ነው አገራችንን እንዳትበትኗት እንዳታፈርሷት የሚል ተገቢ ስጋት ከሶማሌ ክልል መነሳቱን የጠቆሙት ጠ/ሚኒስትር ዐቢይ፤ ኢትዮጵያን ማፍረስ የሚፈልጉ ብዙ ሃይሎች ቢኖሩም ኢትዮጵያ ግን አትፈርስም ብለዋል፡፡

ማፍረስ ቢችሉማ ዓምናም ካቻምናም፣ የዛሬ 20 ዓመትም ሞክረው ነበር፤ ግን አይችሉም ብለዋል - ጠ/ሚኒስትሩ፡፡

ለምንድን ነው ኢትዮጵያ ላይ ጠላቶቻችን የሚረባረቡት ያላችሁ እንደሆነ ተስፋ ስላላት ነው፤ ሲሉም አስረድተዋል፡፡

ጠላቶቻችን ኢትዮጵያን ለማፍረስ በሁሉም መንገድ ሞክረዋል፣ የትኛውም ሙከራ ግን ኢትዮጵያን ማፍረስ አይችልም ያሉት ጠ/ሚኒስትር ዐቢይ አህመድ፤ ኢትዮጵያውያን ሃገራቸውን ስለሚወዱና የመጨረሻው የቁርጥ ጉዳይ ከመጣ ህይወታቸውን ገብረውም ቢሆን እንደ አባቶቻቸው አገር ስለሚያስቀጥሉ ኢትዮጵያን የማፍረስ ፕሮጀክት አይሳካም ብለዋል፡፡

8ኛው ኢትዮ ኸልዝ አውደ ርዕይና ጉባኤ በመጪው ሳምንት በሚሊኒየም አዳራሽ ይካሄዳል  


8ኛው ኢትዮ ኸልዝ አውደ ርዕይና ጉባኤ የአልጀሪያ ብሔራዊ ተሳትፎን ጨምሮ በ12 አገራት መሰረታቸውን ባደረጉ ኩባንያዎች ተሳትፎ በመጪው ሳምንት ከየካቲት 28 – 30 ቀን 2016 ዓ.ም በሚሊኒየም አዳራሽ  እንደሚካሄድ ተገለጸ፡፡

በዚህ አውደ ርዕይና ጉባኤ ላይ ከ4ሺ የሚበልጡ የጤና ባለሙያዎችና የዘርፉ የንግድ ባለድርሻ አካላት ከዓለማቀፍ የዘርፉ መሪዎችና ስመጥር የሃገር ውስጥ ኩባንያዎች ጋር የንግድ ትስስር እንደሚያደርጉ ይጠበቃል ተብሏል፡፡

በዘንድሮው ኹነት በኢትዮጵያ ለመጀመሪያ ጊዜ ከ40 በላይ ነጥብ የሚያሰጡ የተከታታይ የሙያ ማጎልበቻ ሥልጠናዎችና ጉባኤዎች ከ22 የሙያና የዘርፍ ማህበራት ጋር በመተባበር እንደሚሰጥ ተጠቁሟል፡፡

ይህ ልዩ አውደ ርዕይና ጉባኤ አዳዲስ ቴክኖሎጂዎችንና አቅራቢዎችን ለሀገራችን በማስተዋወቅ፣ የቴክኖሎጂና የዕውቀት ሽግግርን በማምጣት ለዘርፉ ልማት በሚደረገው ጥረት ውስጥ ቁልፍ መድረክ መሆኑን ያስመሰከረ ነው የተባለ ሲሆን፤ በዘርፉ ተዋናዮች መካከል የንግድ ልውውጥን በማሳደግና የገበያ ትስስርን በመፍጠር ደረጃ ቀጣይነት ያለው ዕድል የፈጠረ ኹነት እንደሆነ  ተነግሯል፡፡

ኢትዮ ኸልዝ አውደ ርዕይና ጉባኤን ለ8ኛ ጊዜ ያዘጋጀው በበርካታ ዘርፎች የንግድ ትርኢትና አውደ ርዕዮችን በማዘጋጀት የሚታወቀው ፕራና ኢቨንትስ ነው፡፡

መጋቢት 05 ቀን 2016 ዓ/ም ፤ በአዲስ አበባ የገቢ ማሰባሰቢያ ፕሮግራም ያካሂዳል ።
...
ወ/ሮ ሙሉ ግርማይ ተወልደው ያደጉት በቀድሞው አጠራር በወሎ ክፍለ ሀገር በሰቆጣ ከተማ ነው።  በ 1973 ዓ/ም የቀድሞው ኢህዴን / ብአዴን የአሁኑ አዴፓ ፖለቲካ ድርጅት ተመስርቶ ደርግን ለመጣል የትጥቅ ትግሉን በዋግ አካባቢ ሲጀምር እርሳቸውም እንደ ዘመኑ ወጣቶች የደርግን መንግስት አምርረው ይጠሉ ስለነበር የሁለተኛ ደረጃ ትምህርታቸውን አቋርጠው በ 1975 ዓ/ም የትጥቅ ትግሉን ተቀላቀሉ።

የኢትዮጵያ ህዝብ ትግል ከ ጊዜ ወደ ጊዜ እየጠነከረ ሄዶ በ 1983 ዓ/ም የደርግ መንግስት ከስልጣን ሲባረር ቀደም ሲል ከአራት ድርጅቶች ጥምረት ኢህአዴግ ተብሎ በተመሰረተው ድርጅት የበላይነት የሽግግር መንግስት ሲቋቋም ባለቤታቸው አቶ ታምራት ላይኔ የሽግግር መንግስቱ ጠቅላይ ሚንስትር እርሳቸው ደግሞ የአዲስ አበባ ሪጅን ፅ/ቤት የኢህአዴግ ድርጅት ጉዳይ ሃላፊ ሆነው እየሰሩ ቆዩ።

እርሳቸው እንደሚሉት በ 1989 ዓ/ም " በስልጣን ያለአግባብ መጠቀም " በሚል የፖለቲካ ሴራ ኢህአዴግ አቶ ታምራትን ለእስር እንዲዳረጉ አደረገ። ይህኔ ታዲያ ወ/ሮ ሙሉ በህይዎቴ ይገጥመኛል ብለው ከማይገምቱት ፈተና ላይ ወደቁ። የአቶ ታምራት ሚስት በመሆናቸው  ከስራ ቦታቸው እና ከሃላፊነታቸው ያለአንዳች ርህራሄ ተባረሩ። በወቅቱ ምንም አይነት ገቢ ወይንም ጥሪት ሳይኖራቸው አራት ዓመት ከሆነው የመጀመሪያ ልጃቸው እና የአንድ ወር ጨቅላ ህፃን ከነበረቸው ሁለተኛ ልጃቸው ጋር ሲኖሩበት ከነበረው የመንግስት ቤትም ሳይቀር እንዲወጡ ተደረገ።

ከእለት ወደ እለት ማወከቦች ፣ የማፈን ሙከራዎች፣  ማስፈራሪያዎችና ልዩ ልዩ ፈተናዎች እየጨመሩባቸው ሲሄዱ በ 1992 ዓ/ም ሁለት ልጆቻቸውንና ታናሽ እህታቸውን ይዘው ወደ ኬንያ በግፍ ተሰደዱ።

ከሦስት ዓመታት የኬንያ አስቸጋሪ የስደት ቆይታ በኋላ በ 1995 ዓ/ም ወደ አሜሪካ በስደት እንዲገቡ ተፈቅዶላቸው በኮሎራዶ ግዛት ዴንቨር ከተማ መኖር ጀመሩ ። በአሜሪካን ሀገርም ብቻቸውን ሆነው ልጆቻቸውን እንደሚያሳድግ እናት የጋዝ ማደያ ፣ የልብስ መሸጫ መደብርና የመሳሰሉት እየሰሩ ልጆቻቸውን ማሳደግና ማስተማር ቀጠሉ።

በ 2000 ዓ/ም ባለቤታቸው አቶ ታምራት ላይኔ ከእስር ተፍትተው ወደ አሜሪካን ሀገር በመጡበት ወቅት ወ/ሮ ሙሉ ጋዝ ማደያ ተቀጥረው ይሰሩ እንደነበር ያስታውሳሉ።

ለ አስራ ሁለት ዓመታት ልጆቻቸውን ያለአባት ማሳደጋቸውና ልጆቻቸውም እነዛን ረጅም ዓመታት ያለ አባት ማደጋቸው እርሳቸው ባለፉበት የመከራ ህይዎት ውስጥ የሚያልፉ ልጆችና ዝቅተኛ ገቢ ያላቸው እናቶችን በተለየ መንገድ እንዲያስቡ አደረጋቸው። በሚወዷቸውና የኔ በሚሏቸው ሰዎች መጠላትና መገለል አሳዛኝ የህይዎት ክስተት መሆኑን ተገነዘቡ ። እናም የተቸገረን ሰው ቀርቦ ማፅናናትና መደገፍ ምንያህል የተቀደሰ ተግባር መሆኑን ከህይዎታቸው ተማሩ።

ከዛም የእርሳቸው እና የቤተሰባቸው የመከራ ውጤት የሆነው እንዲሁም ለችግር የተጋለጡ ፤ ወላጆቻቸውን ያጡ ልጆችና መበለቶችን የሚያግዘው ላይፍ ሴንተር ኢትዮጵያ የበጎ አድራጎት ድርጅት በ 2005 ዓ/ም ሊመሰረት ቻለ።

ላይፍ ሴንተር ኢትዮጵያ ፤ በአዲስ አበባ ፣ በአማራ ክልል ዋግህምራ ሰቆጣ ከ400 በላይ መበለቶችንና ከ280 ወላጆቻቸውን ያጡ ለችግር የተጋለጡ ልጆችን በመርዳት ላይ የሚገኝ ድርጅት ሲሆን መጋቢት 05 ቀን 2016 ዓ/ም በከተማችን አዲስ አበባ የገቢ ማሰባሰቢያ ፕሮግራም አዘጋጅቷል ። ሁሉም የማህበረሰብ ክፍል የዚህ የገቢ ማሰባሰቢያ ፕሮግራም በሚችለው ሁሉ አጋር እንዲሆንና ከፍተኛ ችግር ውስጥ ያሉ ሴቶችና ህፃናትን እንዲያግዝ በማዕከሉ በተሰጠው ጋዜጣዊ መግለጫ ላይ ጥሪ ቀርቧል።

በአዲስ አበባ ወሎ ሰፈር ጎርጎሪዮስ አደባባይ ፊት ለፊት የተገነባው ባለ 15 ፎቅ ዓለማቀፍ ሆቴል፤ የፊታችን ቅዳሜ  የካቲት 23 ቀን 2016 ዓ.ም እንደሚመረቅ ተገለጸ፡፡
ለግንባታ 7 ዓመት የፈጀውና የኩራዝ ወንዝ ኃ.የተ.የግ. ድርጅት አጠቃላይ ፕሮጀክት አንደኛው እህት ኩባንያው ነው የተባለው ሽታዬ ስዊት ሆቴል፤ አባት አርበኞች፣ የመንግሥት ባለሥልጣናትና አምባሳደሮች በተገኙበት ይመረቃል ነው የተባለው፡፡
በ600 ካ.ሜ ቦታ ላይ ያረፈው ሆቴሉ G†15 ከአንድ ቤዝመንት ጋር ያለው ሲሆን፤ በቂ የመኪና ማቆምያ ቦታም ያካተተ መሆኑ ተጠቁሟል፡፡
ሆቴሉ የራሳቸው ማብሰያ ክፍሎች ያላቸው ሰፋፊ ምቹና ዘመኑ ያፈራቸውን መገልገያዎች የያዙ መኝታ ክፍሎች ያሉት ሲሆን፤ ለየት የሚያደርገውም የፔንት ሃውስ ክፍል ምርጫ ያለው ነው ተብሏል፡፡
የባህል ምግብ አዳራሽ፣ የመዋኛ ሥፍራና የሰርግ ስብሰባ አዳራሾች ያካተተው ሽታዬ ስዊት ሆቴል፤ ከ200 በላይ ለሚሆኑ ዜጎች የሥራ ዕድል እንደሚፈጥር ተነግሯል፡፡
በሆቴሉ የምረቃ ሥነስርዓት  ላይ ለአባት አርበኞች ምስጋናና ዕውቅና እንደሚሰጥ ታውቋል፡፡

አንድ ንጉሥ አንድ ብልህ አጫዋች ነበራቸው። በየጊዜው ከሚመክራቸው ምክር መካከል ሰሞኑን የነገራቸውን ለመቀበል ከብዷቸዋል። ሰሞኑን የመከራቸው “ከወዳጆችዎ ይልቅ፣ ስለርስዎ ድክመት ዕውነቱን የሚነግሩዎ ጠላቶችዎ ናቸውና አዳምጧቸው” የሚል ነበር። ንጉሡ አላመኑበትም። ስለዚህ ለማረጋገጥ መዘዋወር ጀመሩ።
ንጉሡ በጣም የሚፈሩና አይበገሬ ነኝ የሚሉ ናቸው። በሄዱበት ቦታ ሁሉ የሚያገኟቸውን መኳንንቶች “እስቲ ስለ እኔ ጉድለት ንገሩኝ?” ይሉና ይጠይቃሉ።
“ንጉሥ ሆይ! እርስዎ ላይ እንዴት አይነት ሰው ነው ጉድለት ሊያገኝ የሚችለው። ደግሞ እርስዎ ምን ይወጣልዎታል!” ይሏቸዋል።
ቀጥለው ወደ ሠራዊታቸው ይሄዱና፤
“ምን እንከን አለብኝ? እስቲ ስለራሴ ንገሩኝ?” ይላሉ።
ከሠራዊታቸው ታማኙ ባለሟል ብድግ ብሎ፣
“ንጉሥ ሆይ! እርስዎ ከቁመናዎ ጀምሮ፣ ለጀግንነትዎ፣ ለዕውቀትዎ፣ ለዓለም ተደማጭነትዎ ምን የሚቀነስ የሚወጣልዎ ነገር አለብዎ!” ይላቸዋል። እንዲህ ከርመው አንድ ቀን በአጋጣሚ ከጠላቶቻቸው ጋር በሚሲዮን ይቀመጣሉ። አጠገባቸው የተቀመጠው ቀንደኛው ባላንጣቸው ቀስ ብሎ፤
“ስሙ ንጉሥ፤ ሲናገሩ አፍዎት መጥፎ ጠረን ያመጣል” ይላቸዋል።
ንጉሱ ይናደዳሉ። “እንዴት እስከዛሬ አንድ ወዳጄ ይሄን አልነገረኝም? እንዲህ በአደባባይ እንድጋለጥ ያደረጉኝ ወዳጆቼ ናቸው! ቆይ ግድ የለም! ባልሰራላቸው!” ይላሉ በሆዳቸው። ስብሰባውን እንደጨረሱ ሲገሰግሱ ወደ ቤተ-መንግስታቸው ይሄዱና ንግስቲቱን አስጠርተው፤
“አፌ ጠረን እንዳለው እስከዛሬ ያልነገርሽኝ ለምንድን ነው?” ሲሉ በቁጣ ጠየቁ። ንግስቲቱም፤ በንፁህ ልቦናና በቀናነት፤
“ንጉሥ ሆይ! የሁሉም ንጉስ አፍ እንደ እርስዎ አፍ አይነት ሽታ ያለው መስሎኝ ነው” ሲሉ መለሱ።
ንጉሡም እጅግ የቅርባቸው የሆነችው የገዛ ባለቤታቸው ጉድለታቸውን ሳትነግራቸው፤ ሩቅ የሚኖሩት ጠላቶቻቸው ማወቃቸውን ልብ ሲሉ፤ ያ አስተዋይ አጫዋቻቸው የነገራቸው ቁም ነገር እውነት መሆኑን ተገነዘቡ።
***
ማንኛውም መሪ፣ በማንኛውም ደረጃ ያለ ቢሆን፤ አንድ ሀቅ ልብ ማለት አለበት። ራሱን ብቻ የሚያዳምጥ መሪ፤ ከወዳጆቹ የሚጠብቀው ምንጊዜም ምስጋናን ስለሆነ ጉድለቶቹን የማየትም የመስማትም እድል አያገኝም። ወገኖቹም አይደፍሩትም። እሱም ራሱን አይደፍርም። ይህ ሁሉ የሚሆነው ሁሌ በሰላም ጊዜ በሆነ ባልከፋ። ሁኔታዎች በውጥረትና በችግር በሚሞሉበት ሰዓት ሲመጣ ነው አደጋው። ምክንያቱም የሁኔታዎች መወሳሰብን ተከትለው ሰዎችም ይለወጣሉና ነው። ችግሩ ግን በዚህ ብቻ አያቆምም። መሪውን መስለውና አክለው ማደግ ሲመኙ የቆዩ ባለሟሎቹና ተከታዮቹ አለማዳመጥ ሰናይ ስነምግባር እየመሰላቸው እነሱም እኩዮቻቸው የሚሉትን አልሰማ ይላሉ። በዚህ ምክንያት ካለመደማመጥ አልፎ፣ የሚፈጠረውን ጩኸት ለመገደብ ካለመቻል ደረጃ ይደረሳል። በየመንበራቸው እንደተቀመጡ በየራሳቸው ደሴት ውስጥ ይዋጣሉ። ውለው አድረውም የታችኞቹ በላይኞቹ ላይ ቅያሜን ያጠነክራሉ። ቀስ በቀስ በተለይ የመረረ የመከፋት ስሜት ውስጥ በገቡ ጊዜ፤ እንደ ሮማው ካሽየስ፣ ባለቃው ላይ ማሴርን፣ ራስን እንደማዳን ሲቆጥሩ፤ ከላይ ወደ ታች ይወርዱ የነበሩ ትእዛዛት ወደ ጎንም፣ ወደ ይም እንዲያመሩ ሲፈለግ፣ ለወትሮው የአለቃውን ድክመት ሁሉ የእኔ ነው እያለ አሜን ይል የነበረው ሁሉ፣ ድርሻ ድርሻችንን እንውሰድ በሚል፤ ሌላውን ማነሳሳትና ብሶቱን ሌላው ላይ ማጋበቱን ይያያዘዋል። ይሄኔ እንደ ሮማው ብሩተስ ያለው በትዕግስት የሚያገኘውን ስልጣን ቄሳርን በማስወገድ ሊፈጽመው እንዲሻ ሲተነኮስ፣ ወይም ሲወነባበድ፣ ነገር የተገላቢጦሽ ይሆናል። ቄሳር በመሞቻው “አንተም ብሩተስ?” ያለበት ሰዓት የሚመጣ እንግዲህ ያኔ ነው።በተለይ ስልጣንን በዲሞክራሲያዊ መንገድ የመጋራት ልምድ በሌለበት እንደ እኛ ባለው አገር ብርቱ ጥንቃቄ የሚጠይቀው፣ በወንበሩ ዙሪያ አስፈላጊ ትዕግስትና መቻቻል አለመኖር ነው። መተማመን እንዲኖር ሀሳብን መግለጽ ያስፈልጋል። ለዚህ ደግሞ ነጻነቱ አስፈላጊ ነው። ሀሳብን የመግለጽ ነጻነት በሀቅና ከልብ ካልታመነበት፤ “ለብ ለብ ዲሞክራሲ” “ገባ ያለው ዲሞክራሲ” እና “ስፔሻል ዲሞክራሲ” እያልን እንድንከፋፍል ልንገደድ ነው። “አካሄዱ ፍጻሜውን ያሳያል” እንዳንል፤ አባይን ጭብጦዬን ከቀማኝ ወዲህ አላምነውም፤ የሚሉ ወገኖች ይሟገቱናል። የለም “ግቡ አካሄድን ያሳያል” - የትም ፍጪው ዱቄቱን አምጭው ነው ነገሩ- ለሚሉት ደግሞ ካልታዘልኩ አላምንም፣ ስንቱ ሥልጣን ላይ ከወጣ በኋላ አይደል ወይ መላው የጠፋው የሚሉ ይኖራሉ። ሁኔታዎችን አጣጥመን መጓዝ የሚያስፈልገን ለዚህ ነው። የሚያግባባንን መንገድ ከንፍቀ-ክበባችን ውጭም ቢሆን ማዳመጥ፣ ከባላንጣዎቻችንም ቢሆን መማር፣ ሁሌ ከመተላለፍ አንዳንዴ “ምን ይሆን?” ብሎ ለሌሎች ሀሳብ ትንሽ እድሜ መለገስ፤ ቀስ በቀስ ግትርነታችንን ሊያረግበው ይችላል።
አለንልህ ያልነውንና በእርሱም ትከሻ ለስልጣን የበቃንለትን፣ ከቀን በኋላ ከእርሱ እጅ የማንወጣውን ህዝብ ማዳመጥ እንደሚኖርብን እንድናስብም ፋታ ይኖረናል።
ስለሌላው ውሸት እንጂ እውነት በተናገርን ቁጥር፣ ስለሌላው ድክመት እንጂ አንድ አንኳር ጥንካሬ እንኳን ባነሳን ቁጥር፣ እኛ ብቻ ሀቀኛ፣ እኛ ብቻ ጠንካራ እያልን እንገበዛለን። ይህ ደግሞ ስለራሳችን እውነተኛ ገጽታ እናዳናውቅ ያደርገናል። የእኛኑ ቅኝት የሚያዳምጡ ወገኖቻችንና ደጋፊዎቻችን እውነተኛ ይዘትና ቅርጻችንን አይነግሩንም።
ስለዚህ ከእኛ ውጭ የማዳመጥ ባህል ማዳበር ደግ ነገር ነው- ከ”ጥላትም” ሰፈር ቢሆን። አበው “ክፋትህና ውሸትህ ሲጠፋብህ፤ ጠላትህን አስታውሰኝ በለው” የሚሉት ይሄንኑ ሊያስገነዝቡን ነው፡፡

ኢትዮጵያ የአገራቱ ስምምነት እንቅልፍ እንደማይነሳት ገልፃለች
- በሶማሊያ የሚገኙ ኢትዮጵያውያን ስደተኞች አደጋ ተጋርጦባቸዋል ተባለ

ሶማሊያ በቅርቡ ከቱርክ ጋር የፈፀመችውና የሶማሊያ ፓርላማ ሰሞኑን  ያጸደቀው ወታደራዊ ስምምነት፣ ለአጎራባች አገራት በተለይም ለኢትዮጵያ ትልቅ ስጋት እንደሚጋርጥ ምሁራን ገለፁ። በሁለቱ አገራት መካከል ስምምነቱ የተፈረመው ኢትዮጵያ ከሶማሊላንድ ጋር የመግባቢያ ሰነድ መፈራረሟን ተከትሎ፣ ከሶማሊያ ጋር ውዝግብ ውስጥ በገባች  ማግስት መሆኑ ደግሞ ስጋቱን የባሰ ያደርገዋል  ተብሏል።
ለ10 ዓመታት እንደሚዘልቅ በተነገረለት በዚህ ወታደራዊ ስምምነት፣ ቱርክ ለሶማሊያ የባህር ሃይል ሥልጠናና የቁሳቁስ ድጋፍ እንደምታደርግ ተዘግቧል።
የሶማሊያው ፕሬዚዳንት ሀሰን ሼክ መሀመድ የተፈረመውን ስምምነት አስመልክቶ በሰጡት መግለጫ፤ በሚቀጥሉት አስር ዓመታት ቁጥራቸው በውል ያልተገለጹ የቱርክ የባሕር ኃይል መርከቦችና ወታደሮች በሶማሊያ የባሕር ጠረፍ ውስጥ ሆነው ለአገሪቱ ድጋፍ የሚያደርጉ ሲሆን፤ የሶማሊያ ባሕር ኃይልን መልሶ የማደራጀት ሥራም እንደሚያከናውኑ ጠቁመዋል።
 “የቱርክ ወንድሞቻችን በስምምነቱ መሰረት፣ ባህሮቻችንን ለ10 አመታት ይጠብቃሉ፤ ከ10 አመት በኋላ ጠንካራ የባህር ሃይል እንፈጥራለን” ብለዋል-ፕሬዚዳንቱ።
የስምምነቱ ዝርዝር ይፋ ባይደረግም ቱርክ የሶማሊያን ባህል ሃይል በማሰልጠን የምታስታጥቅ ሲሆን የሶማሊያን የባህር ጠረፍም ለመጠበቅም የራሷን ባህር ሃይል በአካባቢው ታሰማራለች ተብሏል። ስምምነት   በቅርቡ ከአገሪቱ ጋር ውዝግብ ለገባችው ኢትዮጵያ ትልቅ ስጋት እንደሚፈጥር የፖለቲካ ምሁራን ይገልጻሉ። የፖለቲካል ሳይንስ መምህሩ ዶክተር አንተነህ ተስፋዬ ለአዲስ አድማስ በሰጡት አስተያየት፤ ኢትዮጵያ ከተለያዩ ወገኖች ጋር ያለባትን  ውስጣዊ ችግሮች ለመፍታት ዕድል ባላገኘችበት በዚህ ወቅት   ሌላ ግጭት ሊቀሰቅሱ የሚችሉ ጉዳዮች ውስጥ መግባቷ ኃላፊነት የጎደለው ተግባር ነው ሲሉ ተችተዋል።  በተለይ  በሁለቱ አገራት መካከል ግጭት ሊፈጠር ይችላል የሚል ስጋት ባጠላበት በአሁኑ ወቅት፣  አገሪቱ ከቱርክ መንግስት ጋር የፈጸመችው ወታደራዊ ስምምነት ስጋቱን ይበልጥ የሚያባባስ እንደሚያደርገው ተናግረዋል።
ለኢትዮጵያ የባሕር ጠረፍ ያስገኛል የተባለው የመግባቢያ ሠነድ መፈረሙን ተከትሎ፣ በሶማሊያና በሶማሊላንድ በሚኖሩ ኢትዮጵያውያን ላይ ከፍተኛ የደህንነት ስጋት እንደተጋረጠባቸው የጠቆሙት ዶ/ር አንተነህ፤    በተለይም  የሶማሊላንድ  ሁለተኛ  ትልቋ   ከተማ በሆነችው ቦርኦ በሚኖሩ ኢትዮጵያዊያን ላይ   የአካል ጉዳት ለማድረስ፣ ንብረት ለመዝረፍና፣ ቤታቸውን በእሳት ለማቃጠል ሙከራ ተደርጓል  ብለዋል። በሶማሊኛ ቋንቋ “ኢትዮጵያዊ ላይ በተገኘበት እርምጃ ይወሰድበት” የሚል አደገኛ በራሪ ጽሑፍ በሐርጌሳ ከተማ እየተበተነ መሆኑን ተናግረዋል-ወቅቱ  በሶማሊላንድ ለሚገኙ ወደ 50 ሺ የሚጠጉ  ኢትዮጵያውያን እጅግ አደገኛ መሆኑን በመግለፅ።ይህ በእንዲህ እያለ፣  የሶማሌላንድ ፕሬዝዳንት ሙሴ ቢሂ፣ ሶማሊላንድ ከኢትዮጵያ ጋር የተፈራረመችው የባሕር በር የመግባቢያ ስምምነት ተፈጻሚ መኾኑ እንደማይቀር ለአገራቸው መገናኛ ብዙሃን ተናግረዋል። “ሶማሊያ ቱርክን ወይም ግብጽን አጋሯ አድርጋ ብታመጣም፣ ስምምነቱን ተግባራዊ ከመሆን የሚያግደው ነገር የለም” ብለዋል ፕሬዚዳንቱ።
ሰሞኑን በወቅታዊ ጉዳዮች ዙሪያ መግለጫ የሰጡት የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ቃል አቀባይ አምባሳደር መለሰ ዓለም፤ “ሶማሊያና ቱርክ የተፈራረሙት ወታደራዊ ስምምነት ኢትዮጵያ ከሶማሊላንድ ጋር ያደረገችውን መግባቢያ ስምምት ሊጎዳ አይችልም” ብለዋል።
“ሶማሊያም ሆነች ቱርክ ሉአላዊ አገር ናቸው፤ የፈለጉትን ስምምነት ከየትኛውም አገር ጋር የማድረግ መብት አላቸው” ያሉት ቃል አቀባዩ፤ “ኢትዮጵያ ከቱርክ ጋር ጥሩ የሚባል ግንኙነት አላት፤ ይህ ወታደራዊ ስምምነት እንቅልፍ አይነሳንም” ብለዋል።

ወመዘክር አዲስ ያስገነባውን ህንፃ የፊታችን ቅዳሜ ያስመርቃል

•  የተቋሙ የ80ኛ ዓመት ክብረ በዓልም ይከበራል ተብሏል

የኢትዮጵያ ቤተ-መዛግብትና ቤተ-መጻሕፍት አገልግሎት ያስገነባውን ባለ 13 ወለል የቤተመዛግብት ሕንጻ የፊታችን ቅዳሜ የካቲት 16 ቀን 2016 ዓ.ም እንደሚያስመርቅ ተገለጸ።

ከህንፃው ምርቃት ጎን ለጎንም ተቋሙ የተመሰረትበት የ80ኛ ዓመት ክብረ በዓልም በአንድ ላይ ይከበራል ተብሏል፡፡

እነዚህን ሁነቶች ምክንያት በማድረግ በተቋሙ ተመዝግበውና ተጠብቀው የሚገኙና በሌሎች ተባባሪ ተቋማት እጅ የሚገኙ የጽሑፍ ቅርሶች አውደርዕይና ሌሎች ተቋሙን ሊያስተዋውቁ የሚችሉ ክንውኖች እንደሚካሄዱ ለማወቅ ተችሏል፡፡

ዝግጅቶቹ ከእሁድ የካቲት 17 ቀን 2016 ዓ.ም ጀምሮ ለእይታ ክፍት እንደሚሆኑ ተነግሯል፡፡

አንጋፋው ድምፃዊ ጌታቸው ካሳ ህልፈተ ህይወት የተሰማንን ጥልቅ ሀዘን እየገለፅን ለወዳጆቹ እና ቤተሰቦቹ እንዲሁም አድናቂዎቹ መፅናናትን እንመኛለን።

Page 5 of 695