Administrator

Administrator

   ድምፃዊ ሙሉቀን ዳዊት፣ ቃቆ ጌታቸውና ብስራት ሱራፌል በጋራ ያቀነቀኑበት ‹‹መንገደኛ›› የተሰኘ አዲስ የሙዚቃ አልበም ለአድማጭ ቀረበ፡፡ ግጥምና ዜማው በዓለማየሁ ደመቀ፣ በሙሉቀን ዳዊት፣ በጃሉድና በብስራት ሱራፌል የተሰራ ሲሆን ሙዚቃውን ያቀናበረው ካሙዙ ካሳ ነው ተብሏል፡፡ ‹‹መንገደኛ››ን ጨምሮ 13 ዘፈኖች በአልበሙ መካተታቸውም ታውቋል፡፡ በፍቅርና በማህበራዊ ጉዳይ ላይ የሚያጠነጥኑ ዘፈኖች የሚቀነቀኑበት ይኸው አልበም፤ ቴክሼል የተሰኘ ድርጅት ፕሮዱዩስ ያደረገው ሲሆን ቮካል ሪከርድስ እያከፋፈለው እንደሚገኝ ድምፃዊያኑ ለአዲስ አድማስ ገልፀዋል፡፡

   የገጣሚ ሄኖክ ስጦታው ሶስተኛ ስራ የሆነውና ‹‹መንገድ›› የተሰኘው የግጥም መድበል ገበያ ላይ ዋለ፡፡ ገጣሚው የተለያዩ የህይወት ፍልስፍናዎቹን ያሳየባቸው 64 ያህል ግጥሞች የተካተቱ ሲሆን በመፅሀፉ ጀርባ ‹‹ጠፈጠፍ›› በሚል ርዕስ ገጣሚ አበባ ብርሃኑ በማህበራዊ ጉዳይ ላይ የሚያጠነጥኑ ግጥሞቿን በጋራ አሳትማለች፡፡ በመቶ ገፅ የተቀነበበው መፅሀፉ፤ ለአገር ውስጥ በ49 ብር ከ60 ሳንቲም፣ ለውጭ አገራት በ15 ዶላር ለገበያ የቀረበ ሲሆን አከፋፋዩ ጃፋር መፅሐፍት መደብር ነው፡፡ ገጣሚ ሄኖክ ስጦታው በ1994 ዓ.ም ‹‹ነቁጥ››፣ በ2005 ዓ.ም ደግሞ ‹‹ሀ-ሞት›› የተሰኙ የግጥም መጽሐፍትን ለንባብ ማብቃቱ ይታወሳል፡፡

       ከ20 ዓመታት በላይ በሬዲዮ ጋዜጠኝነት፣ በሬድዮ ድራማና ትረካዎች ስራ ላይ የሚታወቀው በድምፁ ብዙዎች የሚያደንቁት ጋዜጠኛ ቢኒያም ደረሰ ድንገት በደረሰበት ትንታ ባለፈው እሁድ ህይወቱ ያለፈ ሲሆን ሰኞ እለት በገነተ ኢየሱስ ቤተክርስቲያን ጓደኞቹ፣ ወዳጅ ዘመዶቹና የሙያ አጋሮቹ በተገኙበት ሥርዓተ ቀብሩ ተፈፅሟል። ጋዜጠኛ ቢኒያም ደረሰ በተለይም በኢትዮጵያ ሬዲዮ የቅዳሜ መዝናኛ ላይ የሬዲዮ ድራማዎችን፣ ጭውውቶችንና ትረካዎችን በማቅረብ ይታወቅ ነበር፡፡  ጋዜጠኛው በባህሪው ጭምትና ሆደ ሰፊ እንደነበር የገለፀው ጓደኛው የፋና ሬዲዮ የመዝናኛ ፕሮግራም አዘጋጅ ጋዜጠኛ ደረጀ አያሌው፤ለስራ እንኳን ተፈልጎ እንደሚገኝና ብዙ ልታይ ልታይ እንደማይል አስታውሶ ብዙ ትኩረትና እድል በማጣት ሳንጠቀምበት ያጣነው ድንቅ ባለሙያ ነው ሲል ምስክርነቱ ሰጥቷል፡፡ ጋዜጠኛ ቢኒያም ደረሰ ላለፉት ሶስት ዓመታት በፋና ብሮድካስቲንግ ኮርፖሬት ይተላለፍ በነበረው ‹‹መሀል ቤት›› የተሰኘ ድራማ በመሪ ተዋናይነት ሰርቶ ማጠናቀቁንና አሁንም በፋና በሚተላለፈው ‹‹እኛን ነው ማየት” የተሰኘ ድራማ ላይ መሪ ተዋናይ ሆኖ እየሰራ እንደነበር ደረጀ ገልጿል፡፡ ቢኒያም ባለትዳርና የሁለት ሴቶች ልጆች አባት እንደነበር ለማወቅ ተችሏል፡፡

     ከዕለታት አንድ ቀን በአንድ መንደር ንብረት ጠፍቶ ሌባውን ለመያዝ አውጫጪኝ ይደረግ ተብሎ፤ የመንደሩ ሰው ሁሉ ተጠርቶ አንድ ዛፍ ሥራ ተሰበሰበ፡፡
ሰብሳቢው- ‹‹ጎበዝ እንዴት አደራችሁ?››
ተሰብሳቢው- ‹‹እግዚአብሔር ይመስገን›› አለ በአንድ ድምፅ
ሰብሳቢውም፤
‹‹ዛሬ እንግዲህ የተሰበሰብነው፤ አንድ ችግር ተፈጥሮ ነው፡፡ እንደምታውቁት በመንደራችን ማንኛውም ንብረት፣ ከብት፣ ገንዘብ ከጠፋ የእኛው መንደር ህዝብ ተሰብስቦ መላ መትቶ፣ አውጣጥቶ፣ ሌባውን እንዲጠቁም ይደረጋል፡፡ ከህዝብ ዐይንና ጆሮ ማንም አያመልጥም፡፡ ዘዴው ከጥንት ጀምረን የምንሠራበት ፍቱን ዘዴ ስለሆነ በቀላሉ የሌባ-ሻይ ጥበቡ ሥራ ላይ ይውላል፡፡
በሉ እንግዲህ ስለጠፋው ወይፈን ምልክት የሚሰጠን ሰው ካለ፤ እጁን አውጥቶ ይነሳና ይናገር?›› አለ፡፡ ከተሰብሳቢዎቹ አንዱ አዛውንት እጃቸውን አወጡ፡፡
‹‹ይናገሩ›› ተባሉና ተፈቀደላቸው፡፡
‹‹ይሄ የጠፋው ወይፈን ቡሬ ነው፡፡ ቤቴ ጎረቤት ስለሆነ ሲወጣ ሲገባ አይቼዋለሁ››
 ሌላው ተነስተው፤
‹‹ዕውነት ነው፡፡ ዐይን የሚገባ፣ የሚያምር ኮርማ ነው፡፡›› አሉ፡፡
ሦስተኛው ሰው፤
‹‹መቼም ወይፈንን የሚያህል ነገር የሚሰርቅ የለመደ ሌባ መሆን አለበት›› ሲሉ፤ ህዝቡ ክፉኛ አገሩመረመ፡፡ ከፊሉ አዲስም የዱሮም ሌባ ሊሆን ይችላል አለ፡፡ ከዚያ ሰው በየተራ የዱሮም ጥርጣሬ፣ አዲስም ጥርጣሬ ያለውን ሰነዘረ፡፡ ሆኖም አንድ ሰው ላይ ለማረፍ ችግር ሆነ፡፡
ሰብሳቢው-ደጋግመው፤
‹‹ጎበዝ! እዚሁ መዋላችን ነው፤ ብትናገሩ ይሻላል›› አሉ፡፡ የሚናገር ጠፋ፡፡ ምሽቱ እየገፋ ነው፡፡ ወደመበተኑ ሆነ፡፡ በመካከል ከተሰበሰበው ህዝብ ውስጥ አንዱ ጎኑ ላለው ወዳጁ፤
‹‹ወዳጄ፤ አደራህን ለማንም አትንገር፤ ወይፈኑን የወሰድኩት እኔ ነኝ›› ይለዋል፡፡
‹‹ወስደህ ምን አደረግኸው?››
‹‹ወዲያ ማዶ ላለው መንደር ሸጥኩት››
‹‹እንግዲያው አንድ መላ ታየኝ››
‹‹ምን ታየህ?››
እጁን አወጣ ባለመላው፡፡ ‹‹ተናገር›› ተባለ፡፡
‹ማዶም፤ ወዲያኛውም መንደር፤ ከዚያ ወዲያ ባለውም መንደር አውጫጪኝ መደረግ አለበት፡፡ በእኛ መንደር ብቻ አውጫጪኝ ተካሂዶ መቆም የለበትም፡፡ ለዛሬው ብንበተን ነው የሚሻለን›› አለ፡፡ ሰብሳቢውም፤
‹‹ጎበዝ! ወይፈናችን ተሻግሯል ማለት ነው! ለዛሬው አውጫጪኙ ያብቃ!›› ብለው በተኑት፡፡
ወይፈኑን የሰረቀው ሰው ግን በጣም ከመጨነቁ የተነሳ ሚሥጥሩን የነገረውን ሰው እግር በእግር፣ የገባበት እየገባ ይናገር ይሆን አይናገር ይሆን እያለ ሚሥጥሩን የያዘውን ሰው ሲከታተል እስከ ዛሬ ይኖራል ይባላል፡፡
** ** **
ዓይነቱ ይለያይ እንጂ ሌብነት ቦቃ የለውም፡፡ የጥንቱ አውጫጪኝ የዛሬ ስሙ ግምገማ ነው፡፡ ዞሮ ዞሮ ሚሥጥሩን ለማውጣጣት ሀቀኝነት ይጠይቃል፡፡ የሆድን በሆድ ይዞ ተፋጦ መዋል ፍሬ ነገሩን ከማግኘት ያቅባል። ቂም በቀል ካለ ግምገማ ግቡን አይመታም፡፡ በቅጡ ብንሰራው ጥሩ ነበር፡፡ በበቂ ትኩረት አልሰጠነውም ነበር፡፡ በቀጣይ የምናስብበት ይሆናል…. እያሉ ሸፋፍኖ ማለፍ ድክመትን ተሸክሞ መጓዝ ነው፡፡ መልኩን ይቀያይር እንጂ ሌብነት አንድ ነው፡፡ ሌብነትን በሂደት ማጣራት ለበጣ ነው የሚመስለው!
ሌብነት ሲያስጨንቅ የሚኖር አባዜ ነው፡፡ ሣር ቅጠሉን ሲጠራጠሩ መኖር ነው፡፡ ይሰውረን! አንድ የማዕከላዊ ምርመራ ድርጅት የዱሮ ባለስልጣን አንድ የተፈታ እስረኛ ውጪ አግኝተው ሦስት ምክሮችን ለገሡት ‹‹1ኛ/ ከፖለቲከኞች ጋር አለመገናኘት 2ኛ/ ፖለቲካ አለመናገር፤ 3ኛውና ዋናው ግን ማንም ፖለቲካ ሲናገር ቢያጋጥምህ አለመስማት፤ ምክንያቱም በእኛ ግምት መስማት አደገኛ ወንጀል ነው-ለምን ቢሉ የሰማኸውን የት አረግኸው? የሚል ጥያቄ ያስነሳልና! ሄደህ አንዱ ጋ መተንፈስህ አይቀርም ተብለህ ከመጠርጠር አታመልጣትም! ስለዚህ ከሁሉም ክፉ ወንጀል መስማት ነው! ጆሮህን ድፍን አድርገህ መቀመጥ ምን ይጎዳሃል?!›› አሉት፡፡ የምንሰማው ሁሉ ለጥፋት የሚዳርግ አደገኛ ነገር ነው ብሎ የሚያስብ ለጥርጣሬ እንደተዳረገ ይኖራል፡፡ ቁም ነገሩ ግን የሚሰማ ነገር አለ ወይ? ነው፡፡ በብዛት ተደጋግመው የሚነገሩ ነገሮች በጣም ከመለመዳቸው የተነሳ እንኳንስ ቁም ነገራቸው ጣዕማቸውም ይጠፋል፡፡  በዛሬው ዘመን የሁሉ ነገር መጠቅለያ፤ ‹‹ህዝቡ የሚለውን በወቅቱ በትክልል አላዳመጥነውም ወይም ከናካቴው ጆሮ አልሰጠነውም ነበር›› የሚል ነው፡፡ አሁን ድንገት ጆሮአችን ተከፈተ ዓይነት ይስሙላም ያለው ይመስላል፡፡
‹‹ካለአቅሟ ካፒታሊዝም አስታቅፈው ካልወለድሽ ብለው ሲያማምጧት ከነሶሻሊዝሙም አስወረዳት›› እንደተባለው ነው፡፡ አቅማችንን እንመርምር፡፡ ዘልማድ ትተን ጥናታዊ አካሄድን እንያዝ ጥናታዊ አካሄድን የያዘ ሥርዓት የመገምገሚያም ወግና ደንብ አብሮ ያስቀምጣልና እከክልኝ ልከክልህም፣ የአብዬን እከክ እምዬ ላይ ልክክም ሆነ ሀሳዊ- ተዋናይነት ቦታ አይኖራቸውም፡፡ ፔትሮስ ጊዮርጊስ ለራስ አሉላ የፃፈውን ደብዳቤም አንርሳ፡-
‹‹ታሪክ አላነበቡም እንጂ ፈረንጅና ቁንቁን አንድ ነው፡፡ ቁንቁን ከትል ሁሉ ያንሳል፡፡ ነገር ግን ታላቁን ግንድ በልቶ፣ አድርቆ ይጥለዋል፡፡ እነዚህም መጀመሪያ በንግድ ስም ይመጡና ጥቂት በጥቂት እየገቡ የሰውን አገር ይወርሳሉ፡፡ ስለዚህ አሁን ቶሎ ደብድቧቸው፤ ይለቁ፡፡ አለዚያ አገርም መጥፋቱ ነው፡፡… ዛፍ ሳያድግ በእግር ጣት  ይነጫል፡፡ ካደገ በኋላ ግን ብዙ መጋዝና መጥረቢያ ያስፈልገዋል፡፡ እንደዚሁ የሞራ ግልገል ክንፉ ሳያድግ የስድስት ዓመት ልጅ ከዛፍ አውርዶ ሲጫወትበት ይውላል፣ ክንፉ ካደገ በኋላ ግን ከሰው እጅ ሥጋ ነጥቆ እስከ አየር ይወጣልና የሚያገኘው የለም፡፡ እንደዚሁም እነዚህ ናቸውና ለአገርዎ፤ ለግዛትዎ፣ ለጠጅዎ፣ ለጮማዎ ከሁሉም ይልቅ ለታላቅ ክብርዎ ይሞክሩ›› (ባህሩ ዘውዴ)
ምሁራንም ሚናቸው አይናቄ ነው፡፡ ምሁራንን ማዳመጥ በጎ ነገር ነው፡፡ እንደ ሩሲያ ምሁራን ‹‹ማነው ባለ አባዜው?›› ፤ ‹‹ምን መደረግ አለበት?›› ወይም ‹‹የህዝቡ ወዳጆች እነማናቸው?›› የሚሉ ፀሀፍት ማስፈልጋቸውን እናስተውል!
ለሁሉ ጥያቄ አንድ መጠቅለያ (ፓኮ) ፍለጋ፤ ሁለንተናዊ መድህን (Panacea) አድርጎም ሙሉ በሙሉ መቀበል፤ ትንተናዊ አቅጣጫዎችን እንዳናይ ይገድበናል፡፡ ከተለመዱት መጠቅለያዎች እንደ ‹‹መልካም አስተዳደር››፤ ‹‹ኪራይ ሰብሳቢነት›› ወዘተ ብሎ አለማቆም ብልህነት ነው፡፡ ይሄው ዛሬ ብዙ ያልተመረመሩ የህዝብ ችግሮች ብቅ ማለታቸውን እያመንን ነው፡፡ ራስ-ፍተሻው ይቀጥል! የህዝብን ድምፅ እንደ ባህል መያዝ ዋና ነገር ሲሆን ብዙ ድካም የሌበት ነው፡፡ የሚጠይቀን አንድ ጉዳይ ብቻ ነው- ቀናነት! በቀናነት ጥፋታችንን ማመን! በቀናነት ወገናዊነታችንን ትተን መጓዝ፡፡ መነሳት ያለበትን ሹም ማንሳት፤ በቀናነት እዚህኛው ሥልጣን ላይ ድክመቱ በይፋ የታየውን  ሰው ሌላ ቦታ አለመሾም! በቀናነት ‹‹እንደተጠበቀው አይደለም›› የሚልን ሽባ ሰበብ (Lame excuse) መተው፡፡ ምክንያቱም ለምሳሌ፡- ግብርናው እንደተጠበቀው አይደለም፤ ኢንዱስትሪው እንደተጠበቀው አይደለም፣ ለወጣቱ የተሰጠው ትኩረት እንደጠበቀው አይደለም….›› ይሄ ሄዶ ሄዶ ‹‹እኛም እንደጠበቅነው አይደለንም›› እንዳይሆን መጨረሻውን ማስተዋል አለብን፡፡ ሲደጋገሙ ወደ ፌዝነት የሚለወጡ ብዙ ናቸው፡፡ ለምሳሌ፤ ‹‹ለእግረኛ ቅድሚያ ባለመስጠት….›› ዓይነት፡፡ ‹‹የመልካም አስተዳደር›› አይነት … ወዘተ Stereotype እንደሚሉት ፈረንጆቹ፡፡ በውጥረትና በስጋት እርስ በርስ በመወጣጠር፣ በመወሻሸት፣ የተሳተ መረጃ በመስጠት፣ አላየንም አልሰማንም በማለት… ያለወቅቱ መፍትሔ እንፈጥራለን ብሎ መሯሯጥ ከንቱ ነው፡፡ እንደ እውነቱ ከሆነ እንደ ሀገራችን የዛሬ ወቅታዊ ሁኔታ ዐይን-ከፋች ሁኔታ የለም፡፡ ይህን ሁኔታ በግልፅ የሚያፀኸልን ‹‹ዕንቁላሉን ስለሰበርከው ጫጩት አታገኝም፡፡ በራሱ ሙቀት መፈልፈል አለበት!›› የሚለው አባባል ነው፡፡ ልብ ያለን ልብ እንበል!!

‹‹የህዝቡ ጥያቄ የስርአትና የፖሊሲ ለውጥ ነው››

   በተሃድሶ ግምገማ ላይ ከሚገኙት አራቱ የኢህአዴግ ድርጅቶች ኦህዴድ ሊቀመናብርቱን ሰሞኑን ከሃላፊነት ያነሰ  ሲሆን  ተቃዋሚ ፓርቲዎች  በየትኛውም ደረጃ የሚደረጉ የአመራር ለውጦች ለህዝብ መሰረታዊ ጥያቄ ምላሽ አይሆኑም ብለዋል፡፡
ህዝብ የጠየቀው የስርዓትና የፖሊሲ ለውጥ እንጂ የግለሰቦች መቀያየርን አይደለም፤ ይላሉ ተቃዋሚዎች፡፡
የኢትዮጵያውያን ዲሞክራሲያዊ ፓርቲ (ኢዴፓ) ፕሬዚዳንት ዶ/ር ጫኔ ከበደ፤ የገዥውን ፓርቲ ተሃድሶ ብቻ ሳይሆን ሁሉም አስተሳሰቦች የተካተቱበት የፖሊሲ ለውጦች ነው የጠየቅነው ብለው፡፡ አሁን  ባለው ፖሊሲ ላይ ግለሰቦችን መለዋወጥ ተሃድሶ እንደማይሆን ተናግረዋል፡፡ ‹‹የህዝቡ ጥያቄም የአመራሮች መለዋወጥ›› አይደለም ያሉት ዶ/ር ጫኔ፤ ተሃድሶው በዚህ መልኩ ከቀጠለ ምንም ለውጥ አያመጣም፤ የህዝቡንም ጥያቄ በዚህ መንገድ መመለስ አይቻልም ብለዋል፡፡
በኦሮሚያ የኦህዴድ አመራሮች መቀያየራቸው ሌሎቹ ድርጅቶችም ከዚህ የተለየ አጀንዳ እንደሌላቸው ያሳያል፡፡ ያሉት ፕሬዚዳንቱ፤ በኢዴፓ እምነት ይህ አካሄድ የበለጠ የህዝበን ጥያቄ የማፈኛ መንገድ ነው ብለዋል፡፡ አዴፓ አሁንም ብቸኛው መፍትሄ የብሄራዊ እርቅ መድረክ ማዘጋጀት ነው የሚል አቋም እንዳለውም ዶ/ር ጫኔ ተናግረዋል፡፡
በመጀመሪያም ቢሆን ህዝብ የአመራር ለውጥ አልጠየቀም ያሉት የሠማያዊ ፓርቲ ሊቀመንበር ኢ/ር ይልቃል ጌትነት በበኩላቸው፤ ‹‹ጥያቄው አጠቃላይ የስርአት ለውጥ ነው›› ብለዋል፡፡ ‹‹ህዝቡ ድርጅቶቹና ፖሊሲያቸው አይወክለንም፤ አያስፈልገንም ነው ያለው፤ ግለሰቦች ይለወጡ አላለም›› ያሉት ኢ/ር ይልቃል፤ ድርጅቶቹ በህዝብ ያልተጠየቁትን ነው መልስ እየሰጠን ነው የሚሉት ብለዋል፡፡
ህዝቡ ጉዳዩ ከግለሰቦች ሳይሆን ከስርአቱ ጋር ነው፤ የሚሉት የኦሮሞ ፌዴራሊስት ኮንግረስ (ኦፌኮ) ም/ሊቀመንበርና የመድረክ አመራር አቶ ሙላቱ ገመቹ በበኩላቸው፤ የህዝቡን ጥያቄዎች ያላገናዘበ መፍትሄ ነው ለመስጠት እየተሞከረ ያለው ብለዋል፡፡ የኦሮሞ ህዝብ ከግለሰብ አመራሮች ጋር ችግር የለበትም፤ መሻሻል ያለበት የመንግስት ስርአትና መዋቅር ነው ሲሉ በአፅንኦት የገለፁት አቶ ሙላቱ፤ አሁን የተያዘው የመፍትሄ አቅጣጫ ብዙ ርቀት የሚያስኬድ አይሆንም ብለዋል፡፡
ድርጅቶቹ ከመሰረታዊው የህዝብ ጥያቄ ለመሸሽ በሌላ ጉዳይ ላይ ጊዜያቸውን እያጠፉ ነው፤ ያሉት የመኢአድ ፕሬዚዳንት ዶ/ር በዛብህ ደምሴ፤ ማድረግ ያለባቸው ፖሊሲያቸውን መመርመርና መቀየር ነው ብለዋል፡፡
ለተፈጠሩት ችግሮች በሙሉ ተጠያቂው የመንግስት ፖሊሲ እንጂ የፖሊሲው አስፈፃሚ ግለሰቦች ሊሆኑ አይችሉም የሚሉት ፕሬዚዳንቱ መንግስት የፖሊሲ ማሻሻያዎችን ማድረግ እንዳለበት አሳስበዋል፡፡
አራቱ የኢህአዴግ ድርጅቶች፡- ብአዴን፣ ህውሓት፣ ኦህዴድና  ደኢህዴን በየክልሎቻቸው የተሃድሶ ግምገማ ሲያደርጉ የሰነበቱ ሲሆን በግምገማው በርካታ የአመራር ለውጦች ይጠበቃሉ ተብሏል፡፡ ኦህዴድ የቀድሞ አመራሮቹን አቶ ሙክታር ከድርና ወ/ሮ አስቴር ማሞን ካሃላፊነት አንስቶ በምትካቸው አቶ ለማ መገርሳና ዶ/ር ወርቅነህ ገበየሁን የተካ ሲሆን አቶ ለማ መገርሳ የክልሉ ፕሬዚዳንት እንደሚሆኑ ይጠበቃል፡፡
አዲሱ የኦህዴድ ሊቀመንበር አቶ ለማ መገርሳ በተሾሙ ማግስት በአጭር የሞባይል መልዕክት ለህዝብ ባስተላለፉት መልዕክት፤ ድርጅታቸው የሰፊውን ህዝብ ጥያቄ በየደረጃው ተሃድሶ በማድረግ እንደሚመልስ አስታውቀዋል፡፡ በመቀጠል በላኩት ሌላ የሞባይል መልዕክት ደግሞ፤ ኦህዴድ በህዝብ ፍላጎት ላይ ተመስርቶ ለማድረግ የወሰነው ጥልቅ ተሃድሶ ለሌላውም አርአያ የሚሆን እርምጃ ነው፤ ኦህዴድ ሁሌም ከህዝብ ጎን ይቆማል ብለዋል፡፡


    ማልታ ጊነስ በአይነቱ ልዩ የሆነ የስኬት ቦርድ ውድድር ሰሞኑን በአዲስ ስኬት መዝናኛ ውስጥ አካሄደ፡፡ በ15 ተወዳዳሪዎች መካከል የተካሄደው የስኬት ቦርድ ውድድር፤ በአገራችን አምብዛም ያልተለመደውን የስኬት ስፖርት በስፋት እንዲለመድና ብቃት ያላቸው ተወዳዳሪዎችን ለማፍራት የበኩሉን እገዛ እንደሚያደርግ ተገልጿል።
ከአልኮል ነፃ በሆነው የማልታ ጊነስ ምርት ታጅቦ በተካሄደው በዚህ ውድድር ላይ ከ1-3 የወጡ ተወዳዳሪዎች የማልታ ጊነስ ምርት አምራች በሆነው ዲያጆ ኢትዮጵያ የተዘጋጀላቸውን ሽልማቶች ተቀብለዋል፡፡ ውድድሩ በራሳቸው የሚታማመኑና ብቃት ያላቸው የስኬት ቦርድ ስፖርተኞችን ለማፍራት እንደሚያስችል የማልታ ጊነስ ብራንድ ማናጀር አቶ አቤል አናጋው በውድድሩ ወቅት ተናግረዋል፡፡ በዚሁ የስኬት ቦርድ ስፖርት ውድድር ወቅትም ዲያጆ ኢትዮጵያ ለአዲስ ስኬት ፓርክ የ50ሺህ ብር ድጋፍ አድርጓል፡፡

    ስፔናዊው ቢሊየነር አማኒኮ ኦርቴጋ፤ባለፈው ሳምንት ረቡዕ እና ሃሙስ የማይክሮሶፍቱን መስራች ቢል ጌትስን በመብለጥ ለሁለት ቀናት ብቻ የአለማችን ቁጥር አንድ ቢሊየነር ሆነው እንደነበር ፎርብስ መጽሄት ዘግቧል፡፡ ታ
ዋቂውን ዛራ ጨምሮ የኦርቴጋ ኩባንያዎች ረቡዕ ዕለት የ2.5 በመቶ የአክስዮን ድርሻ ጭማሪ ማሳየታቸውን ተከትሎ፣ የቢሊየነሩ የሃብት መጠን በ1.7 ቢሊዮን ዶላር በማደግ 77.8 ቢሊዮን ዶላር መድረሱንና በዚህም ግለሰቡ የቤል ጌትስን ቦታ በመረከብ የአለማችን ቁጥር አንድ ቢሊየነር መሆን መቻላቸውን ዘገባው ገልጧል፡፡
አርብ ዕለት ማለዳ ግን፣ የእኒሁ ቢሊየነር ኩባንያዎች የአክስዮን ድርሻ በ2.8 በመቶ በመቀነሱ፣ ኦርቴጋ የአለማችን ቀዳሚ ቢሊየነርነቱን ስፍራ ለቢል ጌትስ በማስረከብ ወደ ሁለተኛ ደረጃቸው ተመልሰዋል ተብሏል፡፡
ኦርቴጋ ለመጀመሪያ ጊዜ የአለማችን ቁጥር አንድ ቢሊየነር ለመሆን የቻሉት ባለፈው የፈረንጆች አመት 2015 ጥቅምት ወር ላይ እንደነበር ያስታወሰው ዘገባው፣ በወቅቱ የተጣራ ሃብታቸው 80 ቢሊዮን ዶላር እንደነበርም ጠቅሷል፡፡

      የዛሬን አያድርገውና መስከረም አደይ ነስንሶ በችቦ እየሣቀ ሲመጣ በደስታ የማይፈለቀቅ ከንፈርና ልብ የለም፡፡ ጥሎብኝ እኔም ከመስከረም ጋር ለመሣቅ ነፍሴን ሞርጄ ነበር የምጠብቀው፡፡ ከልጅነቴ ጀምሮ ለአዲስ ዓመት የነበረኝ ፍቅር የትየለሌ ነው፡፡ ሀጫ በረዶ የመሠለው ጄረቴ… ጥርት ያለው ሠማይ፣ ድፍን ጨለማ ሀምሌ ውስጥ ሆኜ በዓይኔ ይመጣ ነበር፡፡… ዘንድሮ ግን ሣቄን የሚያጠፋ፤ ተስፋዬን የሚገፍ፤ ችቦዬን የሚነጥቅ ሀዘን ተፈጠረና የጭጋግ እንቁጣጣሽ አሣለፍኩ፡፡
ፕሮፌሰር መስፍን በ1958 ዓ.ም ተጠይቅ መስከረም ብሎ የፃፉት ግጥም ወደ ልቤ የመጣውም ይሄኔ ነው፤… እኔም በዕለተ እንቁጣጣሽ በJTV ያየሁትን ፕሮግራም አጥቅሼ ስለ ጀግንነትና ሀገር ወዳድነት፤ ስለተስፋና አዲስ ዘመን ጥቂት አሠኘኝ፡፡
መስከረም ተጠየቅ
ተናገር! አትሳቅ
ካልጋ ተቆራኝቶ ታሞ ለሚያጥረው
ወይ አይሞት ወይ አይድን ስቃይ ለታደለው
ለወላድዋ ድሃ ባልዋ ለሞተባት….
በፍርሃት በሥጋት ሥቃይ ለሚበሉት
ለላም አመጣህ ወይ ነፃነትና ሀብት?
ግጥሙ ጠበቅ ያለ ጥያቄ እየጠየቀ ይዘልቃል፡፡ እኔ ግን ወደ ራሴ ጥያቄ እመለሳለሁ፡፡ አዲስ ዓመት ምን አዲስ ነገር ይዞ መጣ ብቻ አይደለም፤እኛስ አዲሱ ዓመት አዲስ ዓይንና ጆሮ እንዲኖረው ምን አደረግን? ዓይነት!... ባለፈው ሰሞን በዚሁ ጋዜጣ ላይ ፖለቲካዊ ንዝረቴን ስለፃፍኩ፣ ዛሬ ወደ ማህበራዊውና ባህላዊው ጉዳይ ዘወር ማለት እፈልጋለሁ፡፡ በተለይ!... የሀገር መውደድ ትርጓሜያችንና በጐነታችንን በተመለከተ፡፡
ለመሆኑ ሀገር ጀግኖች ውስጥ መኖርዋን፣ሀገር በጀግኖች መፈጠርዋንና መቀረፅዋን እንረሣ ይሆን!... ይህንን ስሜትና ጥያቄ የፈጠረብኝ በጆሲ ኢን ዘ ሀውስ ላይ የተመለከትኩት የእንቁጣጣሽ የበዓል ዝግጅት ነው፡፡ ጆሲ ዓውደ ዓመቱን አስመልክቶ ወደ ተዘነጉ የኪነጥበብ ሰዎች ቤት በመሄድ፣ ዘሪቱ ጥላዬ ጨዋቃ፣ ግርማ አምሀ፣ኮሎኔል አብዲስ አጋ ቤተሰቦች ዘንድ ሙክት ይዞ በሥጦታ ታጅቦ፣ አበባየሁ ወይ ለምለም ከሚሉ ልጃገረዶች ጋር በር እያንኳኳ ጀግኖቻችንን ጠይቋል፡፡ በዓለም አደባባይ ያኮራንን የሴ/ኮለኔል አብዲሳ አጋን ታሪክ ፈትሾ፣ ከቤተሰቦቹ ጋር ሲያወጋ፣ በኢትዮጵያዊነቴ አፍሬያለሁ፡፡ ጀግናን ያለማክበር በሽታችን መች ይሆን የሚለቀን? ብዬ ራሴንና ትውልድን ጠይቄያለሁ፡፡
አብዲስ አጋ፤ በኢጣሊያ ሀገር ከእሥር ቤት አምልጦ ከተለያዩ ሀገር ዜጐች ጋር በመሆን የሠራው ጀብዱና ከዕብሪተኛው የሶማሊያ ሰራዊት ጋር ያደረገውን ጀግንነት የተሞላበት ጦርነት አስታውሼ፣ በአንፃሩ ደግሞ ይህንን ሁሉ ውለታ የዋለላት ሀገሩ፤ ለቤተሰቦቹ አንዲትም ጐጆ እንኳን ለመቀለስ ፍቃደኛ ያለመሆንዋ በእጅጉ ዘገነነኝ። ስንት ሕዝብ የዘረፉ ሰዎች ተንደላቅቀው በሚኖሩበት ሀገር፣ ያንን የመሠለ ጀግና ቤተሰቦች አንገታቸውን ደፍተው ሲኖሩ፣ በጊዜው የነበረው ደርግ ብቻ ሣይሆን አጠገቡ የነበሩ ኢትዮጵያዊያንስ እንዴት ዝም ብለው አዩ?-- የሚለው ነገር ጠዘጠዘኝ፡፡… የአብዲሳ አጋ ሕይወት እኮ የኢትዮጵያዊነት ክብር ነው፡፡… ግን አንድ ሁላችንም የምናውቀው በሽታ አለብን፤ በአብዛኛው እርሱ ምን ስለሆነ ነው? … የምትለዋ ዛሬም የተጣባችን ምቀኝነት አለች፡፡… ከሠለጠኑት ሀገራት ሸቀጥ ከምንሰበስብ በጐነትን ብንኮርጅ እንዴት ደግ ነበር… ግና እንዲያ አይደለም፡፡ እርሱ ምን ስለሆነ ነው? ለሚለው መልሱ ቀላል ነው፡፡ ጀግና ስለሆነ መከበር አለበት!!
“ኢትዮጵያዊነት” እያልን ስናቅራራ አፋችን ገደብ የለውም፡፡ ይሁን እንጂ ጀግኖቻችንን አኝከን አኝከን፣ በየደሳሳ ጐጆ ውስጥ ጥለናቸዋል፡፡ ጆሲ ወደተጣሉትና ወደታሰሩት ሰዎች ቤት ጐራ ባለ ቁጥር ነውራችንም አብሮ እየተገለጠ ነው፡፡ አደባባይ ላይ እጃችን ጢስ እስኪያወጣ ያጨበጨብንላቸው ሰዎች፣ሲወድቁ ዘወር ብለን አናያቸውም!... ነገር ግን እኛ ኢትዮጵያዊያን መልካም ነን ብለን በየመጠጥ ቤቱና በየአደባባዩ ስናቅራራ አንደኛ ነን …. ጀግናን ወርውሮ ማቅራራት ምን የሚሉት አመል ነው? ይልቁኑ ለመተቸት አንደኛ ነን፤ሰው የሠራውን ለማሽሟጠጥ ገደብ የለንም፡፡ ሰው ቢሠራ መከራ፣ ባይሠራም መከራ ነው!
ጋዜጠኞች፤ ጀግኖችን የፕሮግራም ማዋዣ ለማድረግ ሩጫችን ዳር የለውም፤… ከዚያ ባለፈ ግን ከሀብታምና ጊዜ ከሰጠው ጋር ሽር ጉድ ከማለት ያለፈ ሕልም የለንም፡፡ ጆሲ ግን ይህንን አድርጐታል፤ የአንድ ቀን እንግዶቹን ጉዳይ ለመፈፀም ስንት ቢሮ እንደደወለ፣ ስንቱን ደጅ እንደጠና እናውቀዋለን፡፡ (ከቢሮ ፀሐፊ ጀምሮ ያለውን ውጣ ውረድ መገመት አያዳግተንም፡፡)
ታዲያ የጆሲ ሥራ እነዚህን የሀገር ቅርሶች ከማገዝ ባሻገር ለቀጣይ ዘመን የሚያመጣው ውጤት አለ፡፡ ያም ዛሬ ጆሲን የሚያዩ ሕፃናትና ወጣቶች፤ ነገ ከኛ  የተሻለ ወገንን የመርዳት፣ ጀግኖችን የማክበር ዘር እንዲፀንሱ ያደርጋል፡፡ መልካም ነገር መሥራት ክብር እንደሆነ ያስተምራል፡፡ እንደ ብዙዎቻችን “ሀገሬ!” እያሉ ከንፈር ላይ ከሚተንን ወሬ የላቀ ውጤት ያመጣል!
የኛ ዘመን ከጀግና ይልቅ ሸቀጥን ያተለቀ፣ ከሀገር ይልቅ ሆድን ማዕከል ያደረገ መሆኑን ለማወቅ መፃሕፍት ማገላበጥ አያስፈልግም፡፡ በየጊዜው ብብታችን ሥር የሚፈለፈሉት “ሆዳሞች” ወገናቸውን ለቅንጣት ኑሮ ብለው እንደሚሸጡ፣ በሚፈስሰው ደሙ ላይ አበባ ነስንሰው እንደሚደንሱ በዐይኖቻችን አይተናል፡፡… ይህ ለኛ ብርቅ አይደለም። … በዚህ መሀል ግን አንዳንዱ ይጮሃል… አንዳንዱ ደወል ይደውላል፡፡ ሆዳሙ ግን መስሚያ የለውም፤… ጆሮው ላይ የሚያፋጨው ሆድ ነው፡፡ መብላትም መጠጣትም ነው፤ የሕይወቱ ግብ፡… ሰውነቱም እንደ በሬ ሥጋ መሸከም ብቻ ነው!!... እዚህ ጋ የዶክተር ፈቃደ አዘዘን ግጥም ልዋስ መሠለኝ፡- “ከበዳ ወደ በዳ” ይላል (“ዳ” ላላ ተደርጋ ትነበብ)
ይጮሃል ደራሲ
ይጮሃል አዝማሪ
ይጮሃል ከያኒ
ግን ማንስ አደምጦ
ኸረ ማንስ ሰምቶ?
ሁሉም እጆሮው ላይ በሆዱ ተኝቶ
አንድ ጣሳ አረቄ አንድ በርሚል ጠላ
ጠጅ ጠጅ አንቡላ
ከአሥራ አሥር ክትፎ ጋር አሥር ኪሎ ሥጋ
ቢጐምድ ቢሰለቅጥ ቢቸልስ ቢለጋ
ይመርጣል ዘመኑ
ጥበብ ለሱ ምኑ?
እውነት ነው፤መብላት መጠጣትና ቅንጦት የሰው ልጅ የኑሮ መለኪያ ሆኗል፡፡ ዶክተር ፈቃደ አዘዘ፤ ከያኔውንም እንደ ተቆርቋሪና ጉበኛ /ሀገር ተቆርቋሪ/ አድርጐ ቆጠረው እንጂ ዋና ባንዳዎቹ፣ ከያኒ ነን ባዮቹ ሆነዋል፡፡ ከስንት አንድ ነው ለሀገሩና ለወገኑ ተቆርቋሪ?... ብዙዎቹ ሆዳቸው አምላካቸው ነው፡፡ … ንባብ የለ፤ እውቀት የለ … ሽቀላ ብቻ… “ሆዳም” ሰው ደግሞ ፍቅር አያውቅም!... ስለዚህ ሀገሩንና ወገኑን ለመሸጥ ቅንጣት አይሳሳም፡፡
… ጆሲ ግን ቢያንስ ጀግኖቻችንን ከየሥርቻው ፈልጐ፣ ሕሊናችንን በፀፀት ጅራፍ ይገርፈዋል፡፡ ይህ ጅራፍ ቀጣዩን ትውልድ እንዳይገርፈው፣ጀግና አክባሪ ትውልድ ያሰለጥንልናል፡፡… ለዛራና ቻንድራ ፍቅር ከንፈሩን የሚመጠውና ለሀገሩ ጉዳይ ባይተዋር የሆነውን ሰው ያነቃቃልናል፡፡ አንዳንድ ሆድ ዓምላኩዎች ይህም ሊያስቀናቸው ይችላል። “ስፖንሰር ፍለጋ ነው!” ብለው በጐ ሥራው ላይ ጥላሸት ከመቀባት አይሳሱም፡፡ እኛ ጋ ግን እንዲህ እንላለን!... አንድ ቀን እንኳን ጀግኖችን መች አስባችሁ ታውቃላችሁ? ባለ ውለታዎችን ማክበርስ መች አስተማራችሁን? …
እኛስ ራሳችን ጀግኖቻችንን የማናከብረው እስከ መቼ ነው? … ብለን ራሳችንን ብንጠይቅ፣ መልሱ፡- እስክንሰለጥን የሚል እንደሆነ ጥርጥር የለኝም። ለጊዜው ግን አንዳች ጨለማ ጋርዶናል፤ አንዳች ዳፍንት ውጦናል!...
ለማንኛውም ሰዓሊና ገጣሚ ገብረ ክርስቶስ ደስታ፤ ”ሀገር” በሚለው ግጥሙ ከተቀኘው ጥቂት ስንኞችን ልዘምር፡-
አገሬ ውበት ነው
ለምለምና ነፋስ የሚጫወትበት
ጸሐይ የሞላበት ቀለም የሞላበት
አገሬ ቆላ ነው ደጋ ወይና ደጋ
እዚያ ብርሃን አለ ሌሊቱ ሲነጋ
ተስፋ አለኝ ይነጋል፡፡ ጀግኖች የሚኮሩበትን ሀገር እንፈጥራለን ብዬም አምናለሁ፡፡       

• ኢህአዴግ እንደ ገዢ ፓርቲ፣በአጠቃላይ ኢትዮጵያ ውስጥ ተቀባይነት አጥቷል
• ለህዝብ ጥያቄ ምላሹ እስራትና ግድያ ከሆነ፣ ችግሩን የበለጠ ያወሳስበዋል
• ተቃዋሚዎችና ምሁራን በገዢው ፓርቲ ፍራቻና ተጽዕኖ ሥር ናቸው
• ኢህአዴግም በያዘው መንገድ ችግሩን ይፈታል የሚልም እምነት የለኝም

በ97 ምርጫ ማግስት የፖለቲካ ቀውሱን ተከትሎ ታስረው ከተፈቱ በኋላ “አንድነት” ፓርቲን በመመስረትና በፕሬዚዳንትነት በመምራት የሚታወቁት አንጋፋው የተቃዋሚ ፓርቲ አመራር ኢ/ር ግዛቸው ሽፈራው፤ላለፉት ሁለት ዓመታት ራሳቸውን ከየትኛውም የፓርቲም ሆነ የፖለቲካ  እንቅስቃሴ አግልለው ቆይተዋል፡፡ በወቅታዊ አገራዊ ጉዳዮች ላይ ሃሳባቸውን ለመስጠት ግን ፈቃደኛ ሆነው፣ከአዲስ አድማስ ጋዜጠኛ አለማየሁ አንበሴ ጋር ተከታዩን ቃለምልልስ አድርገዋል፡፡

   በኦሮሚያና በአማራ ክልል ለወራት የዘለቁት የህዝብ ተቃውሞዎች መንስኤ ምንድን ነው ይላሉ?
ኢትዮጵያ አሁን ያለችበት ሁኔታ እጅግ አሳሳቢ ነው፡፡ በአማራና በኦሮሚያ ክልል ባለፈው አመት የታየው ተቃውሞ በኢትዮጵያ የወደፊት የማደግ፣ የመልማትና የህልውና ሁኔታ ላይ ትልቅ ጥያቄ የሚያስነሳ ነው፡፡ ለዚህ ሁሉ ዋናው መንስኤ ባለፉት 25 ዓመታት የዲሞክራሲ፣ የፍትህና የነፃነት እጦት ስለነበረ ነው፡፡ የዲሞክራሲ እጦት ነው የምልበት አንደኛው ማሳያ፣ ኢህአዴግ ያፀደቀውን ህገ መንግስት እንኳ እያከበረ አለመሆኑ ነው፡፡ ከየትኛውም ግለሰብም ሆነ ቡድን በላቀ ሁኔታ ህገ መንግስቱን የተፃረረው ኢህአዴግና የሚመራው መንግስት ነው፡፡ ለዚህ ማስረጃ ጥቀስ ከተባልኩ፣ በኢትዮጵያ ውስጥ ፓርቲዎች እንዲደራጁ ህገ መንግስቱ ይፈቅዳል፤ኢህአዴግ ግን በተግባር ፖለቲካውን የሚያንቀሳቅስ ፓርቲ እንዳይኖር የተለያዩ የአፈና መንገዶችን ሲጠቀም ቆይቷል። በመጀመሪያ አካባቢ በርካታ ፓርቲዎች ነበሩ፤ አሁን የሉም ማለት በሚቻልበት ደረጃ ላይ ናቸው፡፡ ያሉትም ከቢሮ ስራና ከመግለጫ ባሻገር እንቅስቃሴ የላቸውም፡፡ ለነዚህ ፓርቲዎች መቀጨጭ አንዱ መንስኤ በእርግጠኝነት የኢህአዴግ አፈና ነው፡፡ ስለዚህ ህገ መንግስቱ በጥሩ ቋንቋ ያስቀመጠውና የፈቀደው የመደራጀት መብት በኢህአዴግ መንግስት አልተተገበረም፡፡ ሌላው የሚዲያ ሁኔታ ነው፤ ከ97 ምርጫ በፊት በርካታ ነፃ ሚዲያዎች ነበሩ፡፡ አሁን ያሉት ከ5 የሚበልጡ አይደሉም። ብዙ ጋዜጠኞች ተሰደዋል፤ ቀሪዎቹም እስር ቤት ተወርውረዋል፡፡ ስለዚህ የቀሩት ጋዜጠኞች በፍርሃት ራሳቸውን ቆልፈው፣ ራሳቸውን በራሳቸው እየገደቡ የሚንቀሳቀሱ ናቸው፡፡ የመንግስት መገናኛ ብዙሃን የኢህአዴግ ልሳን እስከመሆን ደርሰዋል። የኢትዮጵያን ህዝብ ድምፅ የሚያንፀባርቁ አልሆኑም። የብዙሃኑን ድምፅ አያስተጋቡም፡፡ ይህ ባልሆነበት ሁኔታ ህዝብ የታፈነ ብሶቱን አደባባይ ወጥቶ ቢተነፍስ የሚደንቅ አይሆንም፡፡
ሌላው በሦስተኛ ደረጃ የፍትህ ስርአቱ ድክመት ነው፡፡ ብዙ ፖለቲከኞችና የህዝብ አፍ የሆኑ ጋዜጠኞች ወደ እስር ቤት ተወርውረዋል፡፡ እነ አንዷለም አራጌ፣ እነ እስክንድር ነጋ፣ እነ በቀለ ገርባ፣ እነ ኦላና----እስር ቤት ነው ያሉት፡፡ ይሄን ሁኔታ አብዛኛው ሰው ያውቃል፡፡ ህገ መንግስቱ የሰጣቸውን መብት ሲጠቀሙ ነው አሸባሪ ተብለው እስር ቤት የገቡት፡፡ ሌላው የሲቪል ተቋማትና የሙያ ማህበራት፣ እንደምናውቀው ያለ ኢህአዴግ ቡራኬ መንቀሳቀስ አይችሉም፡፡ ስለዚህ ለዲሞክራሲ ወሳኝ የነበሩት የሲቪክ ተቋማት፣ አሁን በጣም ቀጭጨው ነው ያሉት፡፡ ሌላው የምርጫ አስተዳደሩ ነው። ምርጫው ሙሉ በሙሉ በኢህአዴግ ቁጥጥር ስር ነው ያለው፡፡ ባለፉት 25 ዓመታት የተካሄዱት 5ቱም ምርጫዎች ዲሞክራሲያዊ፣ ፍትሃዊና ነፃ አልነበሩም፡፡ ትንሽ የተለየ ነገር የታየው በ1997 ምርጫ ነው፡፡ ከዚያ በኋላ ሁሉም ነገር ተዘግቷል። ኢህአዴግ መጀመሪያ በ99.6 በመቶ፣ ከዚያ መቶ በመቶ በሆነ ድምጽ አሸነፍኩ አለ፡፡ በምንም መመዘኛ በየትኛውም አለም ታይቶ የማይታወቅ ውጤት ነው የተመዘገበው፡፡ ብዝሃነት ያላት ሀገር ብትሆንም፣ የብዙሃኑ ድምፅ የሚስተጋባበት እድል አልተፈጠረም፤ በምርጫ ስርአቱ፡፡ በፓርላማው አንድ አይነት ቋንቋ ነው የሚነገረው፡፡ ህዝቡ ትክክለኛ ውክልና ኖሮት፣ ድምጹ እየተሰማ አይደለም፡፡ በጣም ዲሞክራሲያዊ የሆኑት የአውሮፓ ሀገሮች እንኳ 50 በመቶ ውጤት ማምጣት እየተሳናቸው፣ የጥምር መንግስት ነው እያቋቋሙ ያሉት፡፡ የህዝብ እምቢተኝነት የመጣው በእነዚህ ምክንያቶች ነው፡፡ መስከረም 30 አዲስ መንግስት በምርጫ ተመርጧል ተብሎ ተመስርቶ፣ተቃውሞው በሁለተኛ ወሩ በህዳር ነው በኦሮሚያ የጀመረው፡፡ እንዴት በ100 ፐርሰንት የተመረጠ መንግስት፣በዚህ ቅጽበት ተቃውሞ ሊገጥመው ቻለ? ይሄ መሰረታዊ ጥያቄ ነው፡፡ በሁለቱም ክልሎች የታዩት ተቃውሞዎች የተቀባይነት ማጣት ማሳያዎች ናቸው፡፡ ድርጅቶቹ እንዴት የህዝብ ተቀባይነት ማግኘት ተሳናቸው? በሁለቱ ክልሎች ህዝብ ኦህዴድና ብአዴንን አልተቀበላቸውም ማለት ነው፡፡ ይሄ የረጅም ጊዜ ብሶቶች ድምር ውጤት ነው፡፡
የህዝብ ተቀባይነት ማጣት እንዴት ተከሰተ?
ሁለቱ ድርጅቶች ኢህአዴግን ወክለው በአማራና በኦሮሚያ ክልል የሚንቀሳቀሱ ናቸው፤ይሁንና ህዝቡን በሚፈልገው መጠን አላረኩትም፡፡ እምነት አልጣለባቸውም፡፡ እነኚህ ድርጅቶች ህዝቡን በነፃነት ማስተዳደር አልቻሉም፡፡ የፌደራል ስርአቱ የሚለው፣ህዝቡ በራሱ ተወካዮች ይተዳደራል ነው። አሁን ጥያቄው፤እነዚህ ድርጅቶች ህዝቡን በአግባቡ ወክለውታል ወይ? የሚለው ነው፡፡ እነዚህ ድርጅቶች የማዕከላዊ መንግስት ተፅዕኖ አለባቸው፡፡ በሌላ በኩል የኢኮኖሚ ፍትሃዊ ተጠቃሚነት ጉዳይና የማንነት ጥያቄም አለ፡፡ የብአዴን አመራሮች፣ ፍላጎታችንን ማሟላት አልቻሉም ነው የሚለው ህዝቡ፡፡ ኦህዴድም የኦሮሚያን ህዝብ ሁለንተናዊ ፍላጎት እያሟላ አይደለም የሚል ነው መሰረታዊ ጥያቄው፡፡
ሁለቱ ድርጅቶች የህዝባቸውን ፍላጎት ማሟላት ያልቻሉበትን ምክንያት ዘርዘር አድርገው ሊነግሩን ይችላሉ?
ራሱ ኢህአዴግ እኮ የተወሰኑ ሰዎችና የህውሓት የበላይነት የሚታይበት ድርጅት ነው፡፡ ይሄ ጥሬ ሃቅ ነው፡፡ የኦሮሚያንና የአማራን ህዝብ የሚወክሉት ፓርቲዎች ከዚህ በመነሳት የሚወክሉትን ህዝብ በእኩል ቁመና በአግባቡ ሊወክሉት አልቻሉም፡፡ በኢኮኖሚ ተጠቃሚነት፣ በተለያዩ መሰረተ ልማቶች ተገቢውን ተጠቃሚነት እያገኙ አለመሆኑን ራሳቸው ይናገራሉ። ኢህአዴግ ውስጥ ዲሞክራሲያዊ አሰራር ስለሌለ፣ የበላይነት ያለው አካል አድራጊ ፈጣሪ ነው የሚሆነው። እነሱ ራሳቸው በቅርቡ ጥሩ አመራር ያገኘ ክልል ጥሩ ይለማል፤ ጥሩ ያላገኘ ይጎዳል ብለዋል፡፡ ይሄ መሸፋፈን ነው፡፡ እነዚህ ክልሎች ራሳቸውን በፈለጉት መንገድ ማስተዳደር ይችላሉ ወይ ሲባል እንደማይችሉ እያየን ነው፤ ህዝቡም ፊት ለፊት እየነገራቸው ነው፡፡ “የህውሓት የበላይነት ይቁም” የሚል ጥያቄ ታዲያ ከየት የመጣ ነው? ምክንያቱ ይሄው ነው፡፡ የበላይነት ያለው አካል፣ በክልሉ ቀርቶ ከክልሉ ውጪም ሁሉን ነገር ለመጠቅለል ፍላጎት ይኖረዋል፡፡
የህዝባዊ ተቃውሞውን ባህሪ እንዴት ገመገሙት?
የህዝቡ እምቢተኝነት አሁን ጎልቶ የወጣው በኦሮሚያና በአማራ አካባቢ ቢሆንም በሌላው አካባቢም ተመሳሳይ ነገር አለ፡፡ መጀመሪያ ኦሮሚያ ነበር፤ ወደ አማራ ሄደ፤ አዲስ አበባም ተሞክሮ ነበር። ይሄ ነገር ሁሉም ጋ የመነሳት አዝማሚያ ያለው ይመስላል፡፡ በደቡብ ኮንሶ አካባቢ ጥያቄዎች አሉ። በአዲስ አበባ አብዛኛው ህዝብ ዘንድ፣መንግስት በሚገባ ሀገር እያስተዳደረ አይደለም የሚል አመለካከት አለ፡፡ ይሄን በዳሰሳ ጥናት ማረጋገጥ ይቻላል፡፡ ጎልቶ የመታየትና ያለመታየት ጉዳይ ነው እንጂ እንደኔ ችግሩ አገር አቀፍ ነው፡፡ እንደ ገዢ ፓርቲ ኢህአዴግ በአጠቃላይ ኢትዮጵያ ውስጥ ተቀባይነት አጥቷል፡፡
ህዝባዊ ተቃውሞው የሚቀጥል ከሆነ፣ መጨረሻው ምን የሚሆን ይመስልዎታል?
እሱ በጣም አሳሳቢ ነው፡፡ ይሄ ይሆናል የሚል ሃሳብ እንደ ማቅረብ እንዳይሆንብኝ እንጂ ችግሩ በጊዜ መፍትሄ ካላገኘ (አያድርገውና) ሀገሪቱ ወደ ግጭት ልትገባ ትችላለች የሚል ፍራቻ አለኝ፡፡ ምክንያቱም የዲሞክራሲ፣ የፍትህ እጦት፣ የኢኮኖሚ ፍትሃዊ ተጠቃሚነት፣ የስራ አጥነትና የብሄረሰብ ግጭት የመሳሰሉት አስጊ ናቸው፡፡ የሀገሪቱን አጠቃላይ የመንግስት አስተዳደር የሚጎዳና የሀገሪቱን ህልውና የሚፈታተን ይመስለኛል፡፡ አሁን ያለው ሁኔታ በሚገባ ካልተስተናገደ ሀገሪቱ አደጋ ላይ ነች ብዬ እገምታለሁ፡፡
መንግስት ለችግሩ መፍትሄ አበጃለሁ እያለ ነው። መንግስት ችግሩን የተረዳበትና የመፍትሄ አሰጣጡን እንዴት ያዩታል?
መንግስት በመሰረቱ ችግሩን አውቆታል፤ የመፍትሄው አቅጣጫ ግን ወቅታዊና ችግሩን ያገናዘበ አይደለም፡፡ መግለጫ አውጥቷል፣ አንጋፋዎቹ አመራሮችም በሚዲያ ተናግረዋል፡፡ ሰዎቹ ችግሩን ያውቁታል፤ ግን አካሄዳቸው ለችግሩ መፍትሄ በሚሰጥ አግባብ አይደለም፡፡ ችግሩን እያወቁ በቀጥታ ለችግሩ መፍትሄ ከመስጠት ይልቅ ሌላ ከችግሩ ጋር የማይገናኝ መፍትሄ ማስቀመጥ፣ የበለጠ ነገር ማወሳሰብና ማባባስ ነው፡፡ መንግስት ችግሩን በተረዳበት መንገድ ትክክለኛ መፍትሄ መስጠት አለበት፡፡ የጉልበት መፍትሄ ዘላቂ አይሆንም፡፡ በኃይል በመሳሪያ፣ በደህንነት የሚሰጥ ምላሽ የህዝብን ጥያቄ አያቆምም፡፡ በመሳሪያ የሚሰጠው ምላሽ ችግሩን ይበልጥ ያባባሰው ይመስለኛል። ለህዝብ ጥያቄ ምላሹ እስራትና ግድያ ከሆነ መፍትሄው ይወሳሰባል፡፡ አሁን የተገደሉት 1ሺ ነው ይባላል፡፡ ጉዳዩ የቁጥር ጉዳይ አይደለም። አንድም ሰው መሞት የለበትም፡፡ ህዝቡ ባዶ እጁን ሰላማዊ ሰልፍ እስከወጣ ድረስ ሰላማዊ መስተንግዶ ማግኘት ህገ መንግስታዊ መብቱ ነው፡፡ ባለፈው ዚምባቡዌ ሰላማዊ ሰልፍ ነበር፤ አንድም ሰው አልሞተም፡፡ በኛ ሀገር ሰላማዊ ሰልፍ ለምንድነው አሳሳቢ የሆነው? ለምንድን ነው አስፈሪ የሚሆነው? የሚሰጡትም ምክንያቶች አንዳንዴ አሳፋሪ ናቸው። ራሳቸው ሰልፈኞቹ ታጥቀዋል ይባላል። ግን በሁለቱም አካባቢዎች፣ ኦሮሚያና ባህርዳር ላይ ያ ሁሉ ሰው ሲሞት የታጠቀ ሰልፈኛ አልነበረም፡፡ ፍቃድ ያልተሰጠው ሰልፍ የሚባል ነገር ደግሞ አለ። ይሄ ህገ መንግስቱን በግልፅ መፃረር ነው፡፡ ፍቃድ አያስፈልግም፤ ማሳወቅ በቂ ነው፡፡ ስለዚህ መንግስት ራሱ ችግሩን በደንብ እያወቀው፣ የሚያስቀምጠው መፍትሄ ግን መስመሩን የሳተ ነው፡፡
አንጋፋ የቀድሞ የኢህአዴግ ታጋዮች (የጦር ጀነራሎች) ሀገሪቱን ከውድቀት ለመታደግ በሚል የመፍትሄ ሃሳቦች እያቀረቡ ነው፡፡ በመፍትሄ ሃሳቦቹ ላይ የእርስዎ አስተያየት ምንድን ነው?
ችግሩ አሳስቧቸው የመፍትሄ ሃሳብ ሲያቀርቡ እያየን ነው፡፡ እነሱም ኢህአዴግ አምባገነን ሆኗል፤ አደጋ ከመምጣቱ በፊት የምርጫ ምህዳሩን አስፍቶ ሁሉም በምርጫው ተሣታፊ መሆን አለበት ብለዋል። መልካም ነገር ነው፤ ቢያንስ ግማሽ መንገድ ሄደዋል፡፡ እነሱ የሚሉት ጠቅለል ተብሎ ሲታይ፣ ኢህአዴግ እንዳለ ሆኖ ጥገናዊ ለውጥ ያድርግ ነው። ግን ህዝቡ በኢህአዴግ ላይ ምን ያህል እምነት አለው? የሚለውን አልተገነዘቡም፡፡ ለዚህ ነው ግማሽ መንገድ ሄደዋል ያልኩት፡፡
ኢህአዴግ በተሃድሶ ከተጋረጡበት ችግሮች የመውጣት ልምድ አለው፤አሁንም ስር ነቀል ተሃድሶ አድርጎ ችግሮችን እንደሚፈታ እየተነገረ ነው፡፡ እርስዎ ምን ይላሉ?
እርግጥ ነው በ1993 ተሃድሶ አካሂደዋል፡፡ በወቅቱ የተካሄደው ተሃድሶ ምክንያቱ፣ የኢትዮ-ኤርትራ ጦርነት የፈጠረውን ልዩነት ያስታከከ ነው እንጅ የህዝብ ቁጣ አልነበረም፤ የስልጣን ሽኩቻ ተሃድሶ ነው ያደረጉት። አሁን ደግሞ ህዝብ እምቢ ሲል ተሃድሶ እናደርጋለን ማለታቸው የእሣት ማጥፋት ዘመቻ ነው፡፡ ችግራቸውን  በሚገባ አልፈተሹም፡፡ የአመራር ችግር እንዳለባቸው ለመገንዘብ 15 አመት ሙሉ ምን አስጠበቃቸው? ተሃድሶ እኮ ችግር ሲመጣ ብቻ አይደለም፤በእቅድ በየጊዜው መደረግ አለበት፡፡  
አንዳንድ ወገኖች ከእንግዲህ ይህ መንግስት አብቅቶለታል ይላሉ፡፡ አሁን የተቀሰቀሰው ተቃውሞ መንግስት እስከመቀየር የሚያደርስ ይመስልዎታል?
በጣም አስቸጋሪ ነው፡፡ እርግጥ ይሄ መንግስት አበቃለት የሚሉ የተለያዩ ወገኖች አሉ፡፡ ግን ይሄ ሁኔታ ከስሜታዊነት የመጣ ይመስለኛል፡፡ ምክንያቱም የመንግስት መዋቅር ደካማ ቢሆንም የመኖር ጉልበት አለው፡፡ ጉልበቱ እስኪያልቅ ሊኖር ይችላል፡፡ አሁን አበቃለት፣ አለቀለት ማለት አያስችልም፡፡ መንግስት ችግሩን ተረድቶ ትክክለኛ መፍትሄ ካልሠጠ ግን ሁኔታዎቹ ወደዚያ ነው የሚያመሩት፡፡
በእንዲህ ያለ የቀውስ ወቅት ተቃዋሚ ፓርቲዎችና ምሁራን ሚናቸው ምን መሆን አለበት?
ይሄን በእውነት በአሳዛኝ መልኩ ነው የማየው። በአጠቃላይ ምሁራኑ ራሳቸውን ከኢትዮጵያ ፖለቲካ አግልለው ነው ያሉት፡፡ ምሁራን ለሃገር እድገትና ለውጥ መሰረት ናቸው፡፡ ይሄ ግን ለኢትዮጵያ ቅንጦት ሆኗል። ከአገሪቱ አሳሳቢ ችግር ራሱን አግልሎ ነው ያለው ምሁሩ። ይህም የሆነበት ምክንያት የዲሞክራሲ እጦት ነው፡፡ የመናገር ነፃነቱን፣ የመደራጀት ነፃነቱን ለመተግበር ምሁሩ ከፍተኛ ፍራቻ አለበት፡፡ ኢህአዴግ አካባቢ ምሁራንን የማሳተፍ ችግር አለ፡፡ ይሄ ነገር ግን ከሃላፊነት ራስን ማሸሽ ነው፡፡ መማር ማለት ትክክለኛ የሆነውንና ያልሆነውን የመለየት ክህሎት መላበስ ነው፡፡ ስለዚህ ትክክል የሆነውን ትክክል፤ ትክክል ያልሆነውን አይደለም ብለው በድፍረት መናገር አለባቸው፡፡
ተቃዋሚ ፓርቲዎችን በተመለከተ በኔ በኩል በተግባር የሚንቀሣቀስ ፓርቲ አለ ብዬ አላምንም። ፓርቲ ማለት ህዝብ የሚያደራጅ፣ ችግር ሲኖር ሠላማዊ ሰልፍ የሚጠራ፣ መንግስትን የሚፎካከር ነው፡፡ ከዚህ አንጻር ፓርቲዎች አሁን ያሉበት ደረጃ እጅግ የቀጨጨ ነው፡፡ ጋዜጣዊ መግለጫ በመስጠት ነው የተወሰኑት፡፡ ለዚህ ሁሉ መንስኤ ግን የገዥው ፓርቲ ተፅዕኖና ፍራቻ ነው፡፡ ተቃዋሚዎችም ምሁራንም አሁን ካላቸው ፍርሃት ተላቀው የሚገባቸውን ሚና መጫወት አለባቸው፡፡  
ብዙዎች አሁን ያለው የሃገሪቱ ሁኔታ በእጅጉ እንደሚያሳስባቸው ይናገራሉ፡፡ እርስዎ መፍትሄው ምንድን ነው ብለው ያስባሉ?
አንዳንድ ሰዎችና ድርጅቶች ከሚሰነዝሯቸው ሃሳቦች መፍትሄ መሠል ነገር አያለሁ፡፡ ግን መንግስት ያንን ተግባራዊ ያደርጋል ወይ? የሚለው የሁሉም ጥያቄ ነው። የሽግግር መንግስት፣ የባለአደራ መንግስት፣ የእርቅ መንግስት የመሣሠሉትና ጀነራሎቹ የሚሰነዝሯቸው የመፍትሄ ሃሳቦች ሁሉ መፍትሄ ሊሆኑ ይችላሉ፡፡ ግን ችግሩ እንዴት ነው የሽግግር መንግስት የሚቋቋመው? እንዴት ነው ባለአደራ መንግስት የሚቋቋመው? በማን አዘጋጅነት ነው የፖለቲካ ውይይት የሚደረገው? የሚሉት ላይ የቀረቡ ማብራሪያዎች የሉም፡፡ የመፍትሄ ሃሳቦቹ የአፈፃፀም ሁኔታ እጅግ ከባድ ነው፡፡ በአብዛኛው ኳሱ ያለው በኢህአዴግ እጅ ነው፡፡ ኢህአዴግ የሽግግር መንግስት ማቋቋም ፍላጎት አለው ወይ? በጭራሽ የሚያስበውም አይመስለኝም፡፡ ምህዳሩን ነፃ ያደርጋል ወይ? አይመስለኝም፡፡ አስተሳሰባቸው ይሄን ለማድረግ አይፈቅድላቸውም፡፡ መፍትሄ በእጃችን ነው የሚል አመለካከት ነው ያላቸው፡፡
እኛ ብቻ ነን የምናውቀው ነው የሚሉት፡፡ ነፃ ምርጫ ይካሄድ የሚለውን የጀነራሎቹን መፍትሄ ምናልባት ይቀበሉታል ብንል እንኳ ምርጫው ገና 4 ዓመት ይቀረዋል፡፡ የህዝቡ ጥያቄዎች እንዴት ነው 4 ዓመት የሚቆዩት? ወይም ምርጫው ወደዚህ መምጣት አለበት። ያንን ለማድረግ ቁርጠኝነት አለ ወይ? እነዚህ ከባድ ጥያቄዎች ናቸው፡፡ ከሁሉም ወገን የሚቀርቡ መፍትሄዎች መልካም ናቸው፤ ግን አተገባበር ላይ ለአፍ እንደሚቀሉት አይሆኑም፡፡ ስለዚህ በኔ ግምት ሁኔታው እየተባባሰ ሊሄድ ይችላል፡፡ ኢህአዴግም በያዘው መንገድ ለህዝብ ጥያቄ መልስ ሰጥቶ፣ ችግሩን ይፈታል የሚልም እምነት የለኝም፡፡ እኔ እንዲህ ነው የምለው መፍትሄ አላስቀምጥም፡፡ አሁን ያለው ሂደት ራሱ፣ የራሱን መፍትሄ ያመጣል የሚል እምነት ነው ያለኝ። መፍትሄው በሂደት ከእንቅስቃሴዎች የሚገኝ ነው የሚሆነው፡፡

ከ292 ሺህ በላይ የአገሪቱ ስደተኞች በኢትዮጵያ ይገኛሉ

      ባለፈው ሳምንት ብቻ ከ11 ሺህ በላይ የሚሆኑ ደቡብ ሱዳናውያን ስደተኞች በጋምቤላ ክልል በኩል ወደ ኢትዮጵያ እንደገቡ የተባበሩት መንግስታት ድርጅት የስደተኞች ኮሚሽን ትናንት ባወጣው መግለጫ አስታወቀ፡፡
በአገሪቱ እየተባባሰ የመጣው ግጭትና ውጥረት በርካታ ዜጎች አገራቸውን ለቀው ወደ ጎረቤት አገራት እንዲሰደዱ እያስገደዳቸው ነው ያለው ኮሚሽኑ፤ ባለፈው ሳምንት በስደት ወደ ኢትዮጵያ የገቡት ከ11 ሺህ በላይ ደቡብ ሱዳናውያን በኢትዮጵያ የሚገኙ የአገሪቱ ስደተኞችን ቁጥር ከ292 ሺህ በላይ እንዳደረሱት አስታውቋል፡፡
አብዛኞቹ ስደተኞች ናስር፣ ማባን፣ ማቲያንግና ማዩት በተባሉት የደቡብ ሱዳን አካባቢዎች የተጠናከረ ወታደራዊ እንቅስቃሴ በማየታቸውና አዲስ ግጭት ይከሰታል ብለው በመስጋት ስደትን የመረጡ ደቡብ ሱዳናውያን እንደሆኑም አስረድቷል፡፡
ባለፈው ሳምንት በጋምቤላ ክልል ድንበር አቋርጠው ወደ ኢትዮጵያ ከገቡት ደቡብ ሱዳናውያን ስደተኞች፤ አብዛኞቹ ሴቶችና ህጻናት ናቸው ያለው ኮሚሽኑ፣ ብዙዎቹም የኑዌር ጎሳ ተወላጆች እንደሆኑና 500 ያህሉ ስደተኞች ያለ ወላጅ ብቻቸውን ስደት የወጡ ህጻናት እንደሆኑ ገልጧል፡፡
በደቡብ ሱዳን የእርስ በእርስ ግጭት ሳቢያ ወደ ጎረቤት አገራት የተሰደዱ የአገሪቱ ዜጎች ቁጥር ከአንድ ሚሊዮን በላይ መድረሱን ያስታወቀው ተቋሙ፤ ከእነዚህም መካከል ከ185 ሺህ በላይ የሚሆኑት ካለፈው ሃምሌ ወር ወዲህ ስደት የወጡ እንደሆኑ አክሎ ገልጿል፡፡