Administrator

Administrator

    ስምንት የምስራቃዊ አውሮፓ አገራት ባለፉት አራት አመታት ብቻ ከ1 ቢሊዮን ፓውንድ በላይ የሚያወጣ የጦር መሳሪያ ለመካከለኛው ምስራቅ አገራት መሸጣቸው በምርመራ መረጋገጡን ዘ ጋርዲያን ዘገበ፡፡
ባልካን ኢንቬስቲጌቲቭ ሪፖርቲንግ ኔትዎርክና ኦርጋናይዝድ ክራይም ኤንድ ኮራፕሽን ሪፖርቲንግ ፕሮጀክት የተባሉ ተቋማት ያወጡትን መረጃ ጠቅሶ ዘገባው እንዳለው፤ ከ8 የምስራቃዊ አውሮፓ አገራት ወደ መካከለኛው ምስራቅ አገራት ከገቡት በሺህዎች የሚቆጠሩ የተለያዩ ከባድና ቀላል የጦር መሳሪያዎች መካከል አብዛኞቹ በእርስ በርስ ጦርነት ወደምትታመሰው ሶርያ ደርሰው ጥቅም ላይ እየዋሉ ይገኛሉ፡፡  የጦር መሳሪያዎቹን የሸጡት አገራት ቦስኒያ፣ ቡልጋሪያ፣ ክሮሺያ፣ ቼክ ሪፐብሊክ፣ ሞንቴኔግሮ፣ ስሎቫኪያ፣ ሰርቢያና ሮማኒያ እንደሆኑ ለአንድ አመት በዘለቀ የተደራጀ ምርመራ መረጋገጡን የጠቆመው ዘገባው፤ አገራቱ እ.ኤ.አ ከ2012 አንስቶ ባሉት አመታት በድምሩ 1 ቢሊዮን ዶላር የሚያወጣ የጦር መሳሪያ ለሳኡዲ አረቢያ፣ ለዮርዳኖስ፣ ለተባበሩት አረብ ኢሜሬትስና ለቱርክ ሸጠዋል ብሏል፡፡ የጦር መሳሪያዎቹ በመካከለኛው ምስራቅ አገራት በሚገኙ አክራሪ ቡድኖች በጥቅም ላይ እየዋሉ እንደሚገኙ መነገሩን የጠቆመው ዘገባው፤ አምነስቲ ኢንተርናሽናልና የአውሮፓ ህብረት ከሽያጩ ጋር በተያያዘ ተቃውሟቸውን ማሰማታቸውንና የህብረቱ ፓርላማ ከፍተኛ ባለስልጣንም አንዳንዶቹ ሽያጮች የአውሮፓ ህብረትን የጦር መሳሪያ ሽያጭ ብሄራዊና አለማቀፍ ህጎች የሚጥሱ ናቸው ማለታቸውን አመልክቷል፡፡ 

“በወረዳ አመራሮች የሚሰሩ ስህተቶች መንግስትን ከፍተኛ ዋጋ እያስከፈለው ነው”

   መንግስት ‹‹ህገ ወጥ›› ያላቸውን ቤቶች ያፈረሠበት መንገድ በአለማቀፍ የሠብአዊ መብቶች ድንጋጌና በህግ ተቀባይነት እንደሌለው የገለጹ የህግ ባለሙያዎች፤ድርጊቱ የህግ ተጠያቂነትን ሊያስከትል እንደሚችል ተናገሩ፡፡ ቤታቸው ለፈረሰባቸው ዜጎች፣መንግስት ተለዋጭ ቤት መስጠት አለበትም ብለዋል - የህግ ባለሙያዎቹ፡፡  
ዓለማቀፍ የሲቪልና የፖለቲካ መብቶች ስምምነት፤ማንኛውም ሰው ደህንነቱ እንዲጠበቅና መኖሪያ ቤቱ እንዲከበር በፅኑ ይደነግጋል ያሉት አለማቀፍ የህግ ባለሙያው ዶ/ር ያዕቆብ ወ/ማርያም፤በተለያዩ የሠብዓዊ መብት ስምምነቶች፣ የመኖሪያ ቤት ጉዳይ በዋናነት ጥበቃ የሚደረግለት መሆኑን ይገልጻሉ፡፡   
‹‹ሠዎች ህገ-ወጥ ቤት ቢሠሩ እንኳን ቤቶቹ ሲሠሩ በዝምታ የታለፉ እንደመሆናቸው በድጋሚ አይፈርሱም›› ያሉት ዶ/ር ያዕቆብ፤ ‹‹በተለያዩ ሃገራት በህገ ወጥ መንገድ ቤት የሠሩ ሰዎች ካሳ ከፍለው ቤቱ ህጋዊ ይሆንላቸዋል” ሲሉ የሌሎች አገራትን ተመክሮ ጠቅሰዋል፡፡ በቅርቡ የአዲስ አበባ አስተዳደር ያፈረሳቸው ቤቶች አፈራረስም የኢትዮጵያንም ሆነ ዓለማቀፍ የሠብዓዊ መብት ድንጋጌዎችን የጣሰና ዜጎችን ያለ አግባብ ለእንግልት የዳረገ ነው የሚሉት የህግ ባለሙያው፤ ‹‹የከተማ አስተዳደሩ የግድ ማፍረስ አለብኝ ካለም በቅድሚያ ቤት ሊያዘጋጅላቸው ወይም ቤት ሊያሰራቸው የሚችል ተመጣጣኝ ካሣ መክፈል ነበረበት፤ይህን አለማድረጉ በሠብአዊ መብት ጥሰት ሊያስጠይቀው ይችላል›› ብለዋል፡፡
“አስተዳደሩ ቤቶቹ ሲሠሩ እያየ ዝም ካለ፣የቤቶቹን መሰራት እንደፈቀደ ይቆጠራል” ያሉት የህግ ባለሙያው፤ነዋሪዎች መብራትና ውሃ የመሳሰሉ መሠረተ ልማቶችን ሲያሟሉ በዝምታ ማለፉ ብቻውን ቤቶቹን ህጋዊ ያደርጋቸዋል ሲሉም ይሞግታሉ፡፡ ቤቶቹ መፍረስ አይገባቸውም ነበር፤ ስለዚህ አስተዳደሩ የፈፀመው ህገ-ወጥ ድርጊት ነው” ብለዋል፡፡
ይህን የአስተዳደሩን ድርጊት ማረም የሚቻለው መንግስት ለተጎጂዎቹ በቂ ካሳ ሲከፍልና ቤት ሰርቶ ሲሰጣቸው ብቻ ነው ያሉት ዶ/ር ያዕቆብ፤‹‹ወቅቱን ባላገናዘበ መልኩ ቤቶችን በጅምላ አፍርሶ ዜጎችን ሜዳ ላይ መጣል አለማቀፍ የሠብአዊ መብት ድንጋጌዎችን ፈፅሞ የተቃረነ ኢ-ሠብአዊ ድርጊት ነው” ብለዋል፡፡ ቤቶቹን በማፍረስ ተግባር ላይ የተሣተፉ ግለሰቦችም ሆኑ ባለስልጣናትም በግላቸው በህግ መጠየቅ እንዳለባቸው ዶ/ር ያዕቆብ ይናገራሉ፡፡
የህግ መምህርና ባለሙያ አቶ ቁምላቸው ዳኜ በበኩላቸው፤የመጠለያ ጉዳይ በአለማቀፍ የሠብአዊ መብት ድንጋጌዎች ውስጥ በህይወት ከመኖር መብት ጋር ተያይዞ የሚታይ መሆኑን ጠቅሰው፣መጠለያን በዚህ መልኩ ማሳጣት የሠብዓዊ መብት ክብርን የመግፈፍ ድርጊት ነው ብለዋል፡፡ አለማቀፉ የሠብአዊ መብት ድንጋጌ፣ የመንግስት በሲቪል መብቶች ላይ ጣልቃ መግባትን እንደሚከለክል የጠቀሱት ባለሙያው፤መንግስት ቤቶቹን ያፈረሠበት መንገድም በዚህ የህግ ጥሰት የሚታይ ነው ሲሉ አሰረድተዋል፡፡
መንግስት ለዜጎች መጠለያ ማቅረብ ካልቻለ ለራሳቸው እንዲሰሩ ሁኔታዎችን ማመቻቸት እንዳለበት የጠቀሱት የህግ ባለሙያው፤ለዚህ አንደኛው መፍትሄ ቤቶቹን ከማፍረስ ይልቅ ወደ ህጋዊ መስመር የሚገቡበትን መንገድ ማመቻቸት ነበር ብለዋል፡፡ ቤቶቹ ሲገነቡ መጀመሪያ ማስቆም ይገባ ነበር ያሉት የህግ ባለሙያው፤ቤቶቹ ከተገነቡ በኋላና ዜጎች በተለያየ መንገድ ህጋዊነት እንዲሰማቸው ከተደረገ በኋላ ማፍረሱ የሠብአዊ መብት ጥሰት ነው ብለዋል፡፡
ግለሰቦቹ መብራት ያስገቡበት፣ ሌሎች የልማት መዋጮዎችን ያወራረዱበት ሰነድ ካላቸውና ወረዳው እያወቀ መሰረተ ልማቶችን ያሟሉ ከሆነ፣ በከፊል ህጋዊ እንደሆኑ ይቆጠራል ያሉት ሌላው ስማቸው እንዳይጠቀስ የፈለጉ የህግ ባለሙያ፤ መንግስት ከዚህ አንፃር መሰረታዊ ስህተቶች መሰራታቸውን አምኖ፣ለተጎጂዎች ተገቢውን ካሳና መጠለያ ሊያቀርብ ይገባል ብለዋል፡፡
ግለሰቦቹ ህገወጥ ናቸው ከተባሉም ግልፅ አማራጮች ተቀምጠው፣በቀጥታ የሚያርፉበት ምትክ መጠለያ ተዘጋጅቶላቸው፣ፍትሃዊ በሆነ ሂደት ተዳኝተው፣ የፍ/ቤት ትዕዛዝ ሲገኝ ብቻ ነው ቤቶች ሊፈርሱ የሚገባው ሲሉ ባለሙያው አስረድተዋል፡፡ “በቂ ማስጠንቀቂያ ሳይሰጠን ነው ቤታችን እንዲፈርስ የተደረገው” የሚለው የዜጎች አቤቱታም ከህግ አንፃር መንግስትን ሊያስጠይቀው ይችላል ብለዋል፤የህግ ባለሙያው፡፡
 የምጣኔ ሀብት ባለሙያው ዶ/ር ቆስጠንጢኖስ በርሄ በበኩላቸው፤መንግስት ቤቶቹን ከማፍረሱ በፊት ደጋግሞ ማሰብና የተለያዩ አማራጮችን ማስቀመጥ ይገባው ነበር ይላሉ፡፡ ህዝቡ መኖሪያ ቤት የሚያገኝበትን መንገድ መንግስት በሚገባ ማሰብ አለበት የሚሉት ዶ/ር ቆስጠንጢኖስ፤ “ሰዎቹ ከገበሬ ላይ ቦታ ገዝተው ቤት ሰርተው የሚኖሩ ከሆነ፣መጠነኛም ቢሆን ገንዘብ ያላቸው መሆኑን የሚያመለክት በመሆኑ፣መንግስት ራሱ ዲዛይን አውጥቶላቸው በህጋዊ መንገድ በማህበር ተደራጅተው ኮንዶሚኒየም እንዲሰሩ ቢያደርግ ለችግሩ መፍትሄ ይሆናል” ብለዋል፡፡  
“ፈረሱ የተባሉት ቤቶች መሰረተ ልማት እስኪሟላላቸው ድረስ ወረዳና ክ/ከተማ ያሉ የመንግስት አካላት የት ነበሩ?” ሲሉ የሚጠይቁት ዶ/ር ቆስጠንጢኖስ፤“በወረዳና ክፍለ ከተማ አመራሮች የሚሰሩ ስህተቶች መንግስትን በከፍተኛ መጠን ዋጋ እያስከፈለው ነው” ብለዋል፡፡
መንግስት በወረዳ ደረጃ በአመራርነት መመደብ ያለበት ብቃት ያላቸውን ሰዎች ሊሆን ይገባል የሚሉት የምጣኔ ሃብት ባለሙያው፤እነዚህ የፈረሱ ቤቶች ይሄን ያህል አመት የቆዩት በተለያየ መንገድ የወረዳ አመራሮች ቢፈቅዱላቸው ነው፤በቤቶቹ ግንባታ ላይ የወረዳ አመራሮች እጅ አለበት ብለዋል፡፡ ቤቶቹ ከመፍረሳቸው በፊት ሌሎች አማራጮች በስፋት ሊታዩ ይገባ ነበር ያሉት ዶ/ር ቆስጠንጢኖስ፤በቀጣይም ቤታቸው የፈረሰባቸው ዜጎች ቤት ማግኘት መቻል አለባቸው፤መንግስትም መፍትሄ ያገኝለታል የሚል እምነት አለኝ ብለዋል፡፡



     የደንበኞች ቀንን ለ3ኛ ጊዜ ያከበረው መሰቦ ሲሚንቶ ፋብሪካ፤የገበያ ድርሻዬን አሳድገውልኛል ፣አጋርም ሆነውኛል ያላቸውን ደንበኞቹን ባለፈው ቅዳሜ ሐምሌ 16 ቀን፣ በባህር ዳር ከተማ ሸለመ፡፡
የሲሚንቶ ምርቶቹን በማጓጓዝና ምርቶቹን በመጠቀም ሁነኛ ደንበኞቼ ናቸው ያላቸውን በርካታ ድርጅቶች ፋብሪካው በተለያዩ ደረጃዎች የሸለመ ሲሆን በትራንስፖርት ዘርፍ የላቀ ተሸላሚ በመሆን ትራንስ ኢትዮጵያ ተጠቃሽ ነው፡፡ ምርቶቹን በማስፋፋት ደግሞ ጉና ትሬዲንግ ተሸልሟል፡፡ ምርቶቹን በመጠቀም የላቀ ሽልማት ከተሰጣቸው መካከል የአዲስ አበባ ቤቶች ግንባታ ፅ/ቤትና የህዳሴውን ግድብ የሚገነባው ሳሊኒ ኮንስትራክሽን በግንባር ቀደምትነት ይጠቀሳሉ፡፡  
የፋብሪካው ስራ አስኪያጅ አቶ ክብረአብ ተወልደ፤ፋብሪካው ዋነኛ ችግሩ ምርቶቹን በራሱ ትራንስፖርት ማጓጓዝ አለመቻሉ መሆኑን ጠቅሰው፣ በቀጣይ በራሱ ትራንስፖርት ለማጓጓዝ  200 ተሽከርካሪዎችን በ877 ሚሊዬን ብር መግዛቱን ተናግረዋል፡፡ እስካሁን ፋብሪካው ምርቶቹን የሚያሰራጨው ከግል ትራንስፖርት ሰጪዎች ጋር ውለታ በመግባት እንደነበርም ሥራ አስኪያጁ አውስተዋል፡፡  
መሰቦ ሲሚንቶ፤ ግልገል ጊቤ 1, 2 እና 3 እንዲሁም ታላቁ ህዳሴ ግድብን ጨምሮ ለመንግስት የተለያዩ ቤቶች ግንባታ ፕሮጀክቶች ምርቶቹን እያቀረበ ሲሆን በሀገሪቱ የገበያ ድርሻውም ወደ 24 በመቶ ከፍ ማለቱን ስራ አስኪያጁ ተናግረዋል፡፡ ፋብሪካው በዓመት 2.3 ሚሊዮን ሜትሪክ ቶን ሲሚንቶ የማምረት አቅም ያለው ሲሆን በየጊዜው አቅሙን የሚያሳድጉ የማስፋፊያ ስራዎችንም እየሰራ ነው ተብሏል፡፡

      ላቀረብነው የጥገኝነት ጥያቄ ተገቢ ምላሽ አልተሰጠንም በሚል በግብጽ ከሚገኘው የተባበሩት መንግስታት ድርጅት የስደተኞች ከፍተኛ ኮሚሽን ቢሮ ፊት ለፊት ባለፈው ማክሰኞ ተቃውሞ ካሰሙ ኢትዮጵያውያን ስደተኞች መካከል ሁለቱ ራሳቸውን በእሳት ማቃጠላቸውን ‹‹ዴይሊ ኒውስ ኢጂፕት›› ዘገበ፡፡
የጥገኝነት ጥያቄ አቅርበው ምላሹን ሲጠባበቁ የቆዩ የኦሮሞ ተወላጆች እንደሆኑ የተነገረላቸው ሁለቱ ኢትዮጵያውያን ስደተኞች፤ 6ኛው ኦክቶበር ሲቲ በሚባለው አካባቢ ከሚገኘው የኮሚሽኑ ቢሮ ፊት ለፊት ራሳቸውን በእሳት አቃጥለዋል ያለው ዘገባው፣ ኢትዮጵያውያኑ ድርጊቱን የፈጸሙት በግብጽ የሚገኙ የኦሮሞ ተወላጆች የጥገኝነት መብታቸው እንዲከበር ካደረጉት ተቃውሞ ጋር በተያያዘ ነው መባሉን ገልጧል፡፡
የተባበሩት መንግስታት ድርጅት የስደተኞች ከፍተኛ ኮሚሽን ረቡዕ ዕለት ባወጣው መግለጫ፤ በተቃውሞው ወቅት ለህልፈተ ህይወት በተዳረገቺው አንዲት የኦሮሞ ተወላጅ  ሞት የተሰማውን ሃዘን እንደገለጸ የጠቆመው ዘገባው፤ ይሄም ሆኖ ግን ኮሚሽኑ ሟቿ የሁለት ልጆች እናት መሆኗን ከመጥቀስ ውጭ ለህልፈተ ህይወት የተዳረገቺው ራሷን አቃጥላ ስለመሆኑ በግልጽ ያለው ነገር እንደሌለ ገልጧል፡፡
“በግብጽ የሚገኙ ጥገኝነት ጠያቂዎች ቁጥር ከፍተኛ ከመሆኑ ጋር በተያያዘ፣ የአቀባበል ስርዓቱ ረጅም ጊዜን የሚወስድ መሆኑ፤ በጥገኝነት ጠያቂ ስደተኞች ላይ ጭንቀትና ተስፋ መቁረጥን እንደሚፈጥር እንገነዘባለን፡፡ ለሁሉም አገር ጥገኝነት ጠያቂዎችና ስደተኞች ፍትሃዊ፣ ወጥና ግልጽነት ያለው አገልግሎት ለመስጠት በትኩረት የሚሰራው ኮሚሽኑ፣ ሁሉም የስደተኛ ማህበረሰብ ይህንን በመገንዘብ በሰላማዊ መንገድ ትብብር እንዲያደርግ ይጠይቃል” ብሏል ኮሚሽኑ ባወጣው መግለጫ፡፡
በግብጽ መዲና ካይሮ የሚገኙ የኦሮሞ ተወላጆች በድረገጾች አማካይነት ያሰራጩት አንድ ቪዲዮ፤ በካይሮ በተደረገው ተቃውሞ ተሳታፊ የነበሩ ሁለት የኦሮሞ ተወላጆች ራሳቸውን በእሳት ማቃጠላቸውን እንደሚያሳይ የጠቆመው ዘገባው፣ ከሁለቱ አንደኛዋም ኮሚሽኑ ባወጣው የሃዘን መግለጫ ላይ ስሟ የተጠቀሰው ሟች እንደሆነች ገልጿል፡፡
የግብጽ የአገር ውስጥ ጉዳይ ሚኒስቴርና ካይሮ የሚገኘው የኢትዮጵያ ኢምባሲ በጉዳዩ ዙሪያ ማብራሪያ እንዲሰጡኝ ጠይቄ ነበር ያለው ‹‹ዴይሊ ኒውስ ኢጂፕት››፣ ሁለቱም አካላት ተፈጸመ ስለተባለው ድርጊት ምንም መረጃ እንደሌላቸው ጠቁመውኛል ሲል ዘግቧል፡፡
 

• ከ60 ሚ.ብር በላይ በሆነ ወጪ ያስገነባቸውን 4 ህንጻዎች ተረክቧል
• የአዲስ አበባን ጨምሮ በ4 ከተሞች ተጨማሪ ህንፃዎች እያስገነባ ነው

  የኢትዮጵያ ፖስታ አገልግሎት ድርጅት የአገልግሎት መስጪያ ጣቢያዎችን ደረጃ ለማሳደግ ባስቀመጠው መርሐ ግብር መሰረት፤ በተለያዩ የሀገሪቱ ክፍሎች ህንፃዎችን በማስገንባት ላይ ሲሆን በአራት ከተሞች ከ60 ሚ. ብር በላይ በሆነ ወጪ ያስገነባቸውን ህንፃዎች መረከቡን አስታውቋል፡፡ በአርባ ምንጭ ባለ ሁለት ወለል፤ በወልቂጤ፣ በነቀምትና በወሊሶ ከተሞች ባለ ሦስት ወለል ህንፃዎች ነው፤የፖስታ አገልግሎት ድርጅት ያስገነባው፡፡
በተጨማሪም በአዲስ አበባ በቱሪስት ሆቴል አካባቢ ባለ አራት ወለል፤ በሽሬ ባለ ሦስት ወለል፣ በደብረ ታቦር ባለ  ሦስት ወለል፣ በወልዲያ ባለ ሦስት ወለል ህንፃ በአጠቃላይ በ45 ሚ. ብር የ4 ሕንፃዎች ግንባታ በማካሄድ ላይ የሚገኝ ሲሆን ግንባታዎቹ በመጪው ዓመት ይጠናቀቃሉ ተብሎ ይጠበቃል፡፡ በተመሳሳይ፤በአዳማ ባለ ሰባት ወለል፣ በአሰላ ባለ አምስት ወለል፣ በጂግጂጋ ባለ አራት ወለል ህንጻዎችን ለማስገንባትም በዝግጅት ላይ መሆኑን ያስታወቀው ድርጅቱ፤በቀጣይም በአዲግራት፣ በዝዋይ፣ በአላማጣና በአሰበ ተፈሪ ከተማዎች የሕንፃ ግንባታ ለማካሄድ ማቀዱን ጠቁሟል፡፡  
ርክክብ የተፈጸመባቸውም ሆነ በግንባታ ላይ ያሉ ህንጻዎች፤ድርጅቱ ለህብረተሰቡ በሚሰጠው ዘርፈ ብዙ አገልግሎቶች ተደራሽነቱን ለማስፋት ያስችለዋል ተብሏል፡፡

      በማረሚያ ቤት አያያዝ ተበድለናል ያሉት የሽብር ተካሳሾቹ የአሮሞ ፌደራሊስት ኮንግረንስ አመራሮችና የሠማያዊ ፓርቲ አባላት ላለፉት 9 ቀናት የረሃብ አድማ ያደረጉ ሲሆን ከማረሚያ ቤቱ ሃላፊዎች ጋር ከተነጋገሩ በኋላ ትናንት መመገብ መጀመራቸውን የረሃብ አድማ ካደረጉት አንዱ የሆኑት የሰማያዊ ፓርቲ የህዝብ ግንኙነት ሃላፊ አቶ ዮናታን ተስፋዬ ለፍ/ቤት አስረድተዋል፡፡
መንግስት በኦሮሚያ ከተቀሠቀሰው ግጭትና ተቃውሞ ጋር በተያያዘ በሽብር ወንጀል ጠርጥሬያቸዋለሁ ሲል ክስ ያቀረበባቸውና በቂሊንቶ ማረሚያ ቤት የሚገኙት የአፌኮ ተ/ም/ሊቀ መንበር አቶ በቀለ ገርባን ጨምሮ የፓርቲ አመራሮች፡- አቶ ገርሣ አያኖ፣ አቶ ደጀኔ ጠፋ እና አቶ አዲሱ ቡላላ እንዲሁም የሰማያዊ ፓርቲ አመራርና አባላት አቶ ዮናታን ተስፋዬ፣ በሌላ ጉዳይ በሽብር የታሰሩት አቶ ብርሃኑ ተ/ያሬድ፣ አቶ ፍቅረ ማርያም አስማማውና ማስረሻ ሰጠኝ በረሃብ አድማ ላይ መሠንበታቸው ታውቋል፡፡
ተከሳሶቹ “በማረሚያ ቤቱ ከሌሎች እስረኞች ተለይተን በጨለማ ክፍል ውስጥ መታሠር የለብንም፤ በቤተሰብም እንዳንጠየቅ ተደርገናል” በሚል የረሀቡን አድማ ላለፉት ማድረጋቸውን የአቶ ዮናታን ተስፋዬ ጠበቃ አቶ ሽብሩ በለጠ ለአዲስ አድማስ አስረድተዋል፡፡
የረሃብ አድማውን ካደረጉት መካከል ትናንት ፍ/ቤት ቀጠሮ መሰረት የነበረው አቶ ዮናታን ተስፋዬ፤ ቆሞ ችሎት መከታተል አለመቻሉን ለፍ/ቤቱ በማስረዳቱ፣ ተቀምጦ ጉዳዩን እንዲከታተል የተደረገ ሲሆን ማክሰኞ እለትም ጉሉኮስ ተሰጥቶት እንደነበር ጠበቃው አስረድተዋል፡፡
በተመሳሳይ እነ አቶ በቀለ ገርባም፤ በረሀቡ መንቀሳቀስ እስኪያቅታቸው ሰውነታቸው መጎዳቱንና ጉሉኮስ እንዲያገኙ መደረጉን ቤተሰቦቻቸው አስረድተዋል፡፡
የማረሚያ ቤት ኃላፊዎች ከትናንት በስቲያ እስረኞቹን በተፈጠረው ችግር ዙሪያ ማነጋገራቸውንና ያላቸውን ጥያቄ ተቀብለው ጉዳዩን “እናየዋለን” ማለታቸውን ተከትሎ፣ ታሳሪዎቹ መመገብ መጀመራቸውን አቶ ዮናታን ለፍ/ቤት ተናግረዋል፡፡

   የበጎ አድራጎት ስራ በግለሰቦች መልካም የማድረግ ጽኑ ፍላጎትና ሃሳብ ላይ ተመስርቶ የሚደረግ ተግባር ሲሆን በሃገራችን ረጅም ታሪክ ያለዉና ለሁሉም ኢትዮጵያዊ የማንነት መለያ ዓርማ ሆኖ የሚያገለግል ሃብት ነዉ:: ይህ የበጎ ተግባር ስራ እንደግለሰቡ ወይም ተቋሙ አቅምና አጠቃላይ ይዘት የሚሰጠዉ የድጋፍ አይነት፤ ብዛትና መጠን ይለያያል፡፡ በመሆኑም ከትንሽ እስከ ትልቅ ከግለሰብ እስከ ተቋም በተለያዬ ሁኔታ ዉስጥ ለሚገኙ ድጋፍ ፈላጊዎች የተለያዬ ድጋፍ ሲደረግ ቆይቷል፡፡
ምናልባትም በሃገራችን በግለሰብ ደረጃ የሚደረጉ ድጋፎች በአይነትም በብዛትም በርካታ እንደሆኑ ቢገመትም ተቌማዊ ቅርጽ ያልያዙ ከመሆናቸዉ አንጻር ሳይንሳዊ በሆነ መልኩ የድጋፉን አይነትና መጠን ለማወቅ ስለማይቻል ይህን ያህል ብሎ በቁጥር ለማስቀመጥ አዳጋች ይሆናል፡፡
ከዚሁ ስራ ጋር በተያያዘ በተለይም የበጎ አድራጎት ድርጅቶችና ማህበራት አሁን ባለንበት ዘመን ሰፊ ድጋፍ እንደሚያደርጉ የሚታመን ሆኖ አመሰራረታቸዉን ስንመለከት ቀደም ባለዉ ጊዜ ረሃብና ድርቅ በተከሰተበት ወቅት ነፍስ የማዳን ተልዕኮ ይዘዉ በመንቀሳቀስ በርካታ ህይወት ማትረፍ የቻሉ ሲሆን ከድርቁ በመለስ መልሶ የማቋቋም ስራዎችንና ብሎም ዘላቂ የልማት ግቦችን በማንገብ የልማት ስራዎችን በስፋት ሲያከናዉኑ ቆይተዋል፤ አሁንም እያከናወኑ ይገኛሉ፡፡ በሃገራችን ኢትዮጵያ በተለይ በ1965 ዓ.ም በወሎና ትግራይ ደርሶ በነበረዉ ከፍተኛ ድርቅ ቁጥራቸዉ በርከት ያለ መንግሰታዊ ያልሆኑ ዕምነት ተኮር ድርጅቶች የማይናቅ ተሳትፎ ከማድረጋቸዉም በላይ ለአሁኑ በሽህ የሚቆጠር የበጎ አድራጎት ድርጅት መፈጠር ምክንያት ነበሩ ለማለት ያስችላል፡፡ ከአስር አመት በኌላ እንደገና በ 1977 ዓ.ም ድርቁ በተመሳሳይ በወሎና ትግራይ አካባቢ በስፋት በመከሰቱ በወቅቱ እነኚህ ድርጅቶች ሰፊ ድጋፍ በማድረጋቸዉ ምንም እንኳ ብዙ ጉዳት ቢደርስም ችግሩን ለመቆጣጠር ተችሏል፡፡
ከላይ በተገለጸዉ ሁኔታ የበጎ አድራጎት ድርጅቶች በሃገራችን ብቅ ብቅ ማለት የጀመሩ ሲሆን በተለይም ከደርግ ዘመን በኌላ በአዲሱ ህገ መንግስት የመደራጀት መብትን በመጠቀም በርካታ የሃገር ዉስጥና የዉጭ በጎ አድራጎት ድርጅቶችና ማህበራት መፈጠር ችለዋል:: ከላይ ለመጥቀስ እንደተሞከረዉ እነኚህ የበጎ አድራጎት ድርጅቶች በተለይም ሃገራዊ የልማት ግቦችንና ዕቅዶችን በማገዝ የመንግስትና የህዝብ የልማት አጋር ሆነዉ የወጡበት ሂደት በግልጽ ይታያል:: በአሁኑ ጊዜ በሃገራችን ከ 3000 የሚልቁ የበጎ አድራጎት ድርጅቶችና ማህበራት የሚገኙ ሲሆን በአሰራር ስርዐት በርካታ ችግሮች ቢገጥሟቸዉም ችግሮቻቸውን ተቋቁመዉ በተለያዬ የልማት፤ የእርዳታና መልሶ ማቋቌም ስራ ላይ ተሰማርተዉ ከፍተኛ አስተዋጽኦ እያደረጉ ይገኛሉ፡፡
የበጎ አድራጎት ድርጅቶችና ማህበራት በተለይም በአሁኑ ሰአት አጠቃላይ የልማት ዕቅዳቸዉን አገሪቱ ካጸደቀችዉ ሁለተኛዉ የአምስት አመት የእድገትና ትራንስፎርሜሽን ዕቅድ ጋር በማጣጣም፤ የዕቅዱን ተፈጻሚነት በየጊዜዉ ከሚመለከታቸዉ የመንግስት መ/ቤቶች ጋር በቅርበት በመገናኘት በመገምገምና የማስተካከያ እርምጃ በመዉሰድ የልማት አጋርነታቸዉን የበለጠ ያሳዩበት ወቅት ቢሆንም ከሚያከናዉኑት ስራ አንጻር ሲታይ ለህዝብ ግልጽ መሆን ያለባቸዉ በርካታ ጉዳዮች ማለትም ከዉጭ ለጋሽ ድርጅቶች የሚያመጡት ገንዘብ፡ በሴክተሩ ዉስጥ ያለዉ የሰዉ ሃይል፡ እንዲሁም በተጨባጭ ለህዝብ የሚያደርጉትና ያደረጉት የልማት ስራ ጥቅል ይዘት ለማህበረሰቡ በሚፈለገዉ መጠን ታዉቌል ለማለት ያስቸግራል።
አንዳንዴም ከዚህ ባለፈ መልኩ የበጎ አድራጎት ድርጅቶችና ማህበራት ለህብረተሰቡ ከሚያበረክቱት አስተዋጽኦ ይልቅ የግለሰብ መጠቀሚያና መክበሪያ ተደርገዉ የመታየታቸዉ ጉዳይ ህዝቡ የተዛባ አመለካከት እንዲይዝ ከማድረጉም ባሻገር የሴክተሩን ገጽታ የሚያበላሽና ጥላሸት የሚቀባ ሆኖ ይታያል፡፡
በዚህ  ጽሁፍ አዘጋጅ - የኢትዮጵያ በጎ አደራጎት ድርጅቶችና ማህበራት መድረክ አመለካከትም በርካታ የበጎ አድራጎት ድርጅቶችና ማህበራት እጅግ ብዙ ዉጤታማ የልማት ስራዎችን የማከናወናቸዉን ያህል የተወሰኑት ደግሞ በጎ ባልሆነ ተግባር ዉስጥ ሲሳተፉ ይስተዋላል፡፡ የኢትዮጵያ በጎ አድራጎት ድርጅቶችና ማህበራት መድረክም ሴክተሩ፤ በአጠቃላይ ተገዥ የሚሆንበትን የስነ ምግባር ደንብ በማዘጋጀትና በማጽደቅ ተግባራዊ እንቅስቃሴ የጀመረ ሲሆን ይህም ጥረት በሴክተሩ ዉስጥ ተጠያቂነትን በማስፈን ግልጽ አሰራር እንዲሰፍን እገዛ ያደርጋል ተብሎ ይታመናል፡፡ በሌላ ወገን ሌሎች ስራቸዉን በትጋትና በቅንነት የሚያከናዉኑትን በማበረታታት፤ ችግሮቻቸዉ ላይ በመወያየትና መፍትሄ በማፈላለግ የተቀላጠፈ የስራ ማዕቀፍ እንዲፈጠርላቸዉ መድረኩ በትጋት ይሰራል፡፡
የበጎ አድራጎት ድርጅቶችና ማህበራት በርካታ ስራ ቢሰሩም ድጋፋቸዉ ለህዝብ በቅጡ ያልታወቀ ከመሆኑ አንጻር የተለያዩ የመገናኛ ብዘሁንን በመጠቀም ስራዎቻቸዉን ለህዝብ ማሳወቅ ተገቢ  በመሆኑ ይህንኑ ስራ መስራት አስፈላጊ ሆኖ ተገኝቷል፡፡ ስለሆነም በሃገራችን የበጎ አድራጎት ድርጅቶች ምን ምን ድጋፍ እንዳደረጉ በተወሰነ መልኩ ከዚህ በታች በተቀመጠዉ ሁኔታ ለመግለጽ ጥረት ተደርጔል፡፡ ከዚህ በላይ በጥቂቱ ለማየት እንደተሞከረዉ በኢትዮጵያ የተለያዬ ይዘት ያላቸዉ በፌደራል ደረጃ ቁጥራቸዉ ከ 3000 የሚልቅ በክልል ደግሞ ከ 1000 የሚበልጡ የበጎ አድራጎት ድርጅቶችና ማህበራት ይገኛሉ፡፡
በእነኚሁ መረጃዎች መሰረት በሃገራችን ያሉ የበጎ አድራጎት ድርጅቶች የሚያተኩሩባቸዉ የልማት ስራዎች በቅደም ተከተል የሚከተለዉን ይመስላሉ፤ ጤና፤ የህጻናት ልማት፤ ትምህርት፤ ማህበራዊ ድጋፍ፡ አቅም ግንባታ፤ ገቢ ማስገኛ አካባቢ ጥበቃ እና እርሻ ስራ ይገኙበታል፡፡ እንደ አዉሮፓ አቆጣጠር በ 2012 በሃገሪቱ በአጠቃላይ 4904 ፕሮጀክቶች የነበሩ ሲሆን ከእነዚህ ዉስጥም 113 በአዲስ አበባ፤ 856 በኦሮሚያ፤ 621 በደቡብ፤ 610 በአማራ፡ 450 በትግራይ፡ 283 በአፋር፤ 267 በድሬዳዋ፤ 59 በቤንሻንጉል፡ 238 በሃረሪ፤ 237 በሶማሌ፤ እንዲሁም 170 ፕሮጀክቶች በጋምቤላ ክልል ተተግብረዋል፡፡ ከዚሁ ጋር በተያያዘ በኢትዮጵያ ዉስጥ ካሉት የጤና ተቌማት ዉስጥ 7% ያህሉ በበጎ አድራጎት ድርጅቶችና ማህበራት ሙሉ ድጋፍ የሚንቀሳቀሱ እንደሆኑ መረጃዎች ይጠቁማሉ፡፡
በተጨማሪም በበጎ አድራጎት ድርጅቶችና ማህበራት ኤጀንሲ ሪፖርት መሰረት  እ.ኤ.አ በ2011፣ 1626 የጤና ፕሮጀክቶች እንደነበሩ የተጠቆመ ሲሆን ወደ 200 የሚጠጉ የበጎ አድራጎት ድርጅቶችና ማህበራት በኤች አይቪ ኤድስ መቆጣጠርና መከላከል ስራ ላይ ተሰማርተዉ እንደነበር ለማወቅ ተችሏል፡፡ በሌላ ሪፖርት እ.ኤ.አ ከ 2004 እስከ 2007 ብር 575 ሚሊዬን ለዉሃ ስራ የዋለ ሲሆን ብር 3 ቢሊዬን ደግሞ በ 336 ፕሮጀክቶች ለእርሻና ተያያዥ ተግባራት ዉሏል፡፡ በተመሳሳይ በሃገሪቱ ካሉ 388 የሙያ ማሰልጠኛ ማዕከላት ዉስጥ 74 የሚሆኑት በበጎ አድራጎት ድርጅቶችና ማህበራት ሙሉ ድጋፍና ቁጥጥር በስራ ላይ የሚገኙ እንደሆኑ መረጃዎች ያመለክታሉ፡፡                                          
በአመታዊ የሲቪል ማህበረሰብ ድርጅቶች ሪፖርት መሰረት እ.ኤ.አ ከ2009 እስከ 2011 ባሉት ጊዚያት ዉስጥ ብር 544,201,454.98 ለዉሃና ተያያዥ ስራዎች ብቻ ተመድቦ ስራ ላይ ዉሏል፡፡
በኢትዮጵያ ዉስጥ ቁጥራቸዉ ከ54 የሚልቅ ህብረቶችና ጥምረቶች ያሉ ሲሆን ለናሙናነት በክርስቲያን ልማትና ተራድዖ ማህበር ህብረት (ሲሲአርዲኤ) ሪፖርት መሰረት እ.ኤ.አ በ2011 10.8 ቢሊዬን ብር በ 320 አባል ድርጅቶች መሰብሰብ የተቻለ ሲሆን፤ አብዛሃኛዉ ገንዘብም ለምግብ ዋስትና፡ ልህጻናት ድጋፍና ለጤና አገልግሎት ስራ በቅደም ተከተል የዋለ መሆኑን መረዳት ተችሏል፡፡ በተመሳሳይ ከአንድ አመት በኃላ በ2012 በተጠናቀረ ሪፖርት ጥቅል ብር 11,841,356,007.87 ለተለያዩ ፕሮጀክቶች ማስፈጸሚያ ዉሏል፡፡
በሌላ በኩል ከኢትዮጵያ ብሄራዊ ባንክ በተገኘ መረጃ መሰረት በ ኢትዮጵያ አቆጣጠር በ 2007 ሙሉ አመትና 2008 – 10 ወር ጊዜ ዉስጥ (አንድ አመት ከአስር ወር ዉስጥ) ከ 2 ቢሊዬን ዶላር (40 ቢሊዬን ብር) በላይ በበጎ አድራጎት ድርጅቶችና ማህበራት የዉጭ ምንዛሬ ገንዘብ ለማግኘት ተችሏል፡፡ 

• ባለፉት 12 ወራት ብቻ፣ 55 ሚ. ዶላር ገቢ አግኝቷል
• ለ117 ታላላቅ ሽልማቶች ታጭቶ፣ በ36 አሸንፏል
    በወቅቱ የአለማችን የሙዚቃ መድረክ ጎልቶ በመውጣት ከፍተኛ ስኬትን የተቀዳጀውና የበርካታ ታላላቅ አለማቀፍ ሽልማቶች ባለቤት ለመሆን የበቃው ትውልደ ኢትዮጵያዊው ድምጻዊ አቤል ተስፋዬ፤ ከአለማችን ከፍተኛ ተከፋይ ዝነኞች ተርታ መሰለፉን ዘ ኢንኩዚተር ዘግቧል፡፡
አለማቀፍ ተወዳጅነትን ያፈራው ድምጻዊ አቤል ተስፋዬ፣ ፎርብስ መጽሄት ከሳምንት በፊት ይፋ ባደረገው የ2016 ከፍተኛ ተከፋይ 100 የዓለማችን ዝነኞች ዝርዝር ውስጥ ለመጀመሪያ ጊዜ ከተካተቱት 15 ዝነኞች መካከል አንዱ መሆኑንና ከእነዚህ መካከልም ከፍተኛውን ገቢ ያገኘው እሱ እንደሆነ የጠቆመው ዘገባው፣ የ25 አመቱ ድምጻዊ አቤል ባለፉት 12 ወራት ብቻ 55 ሚሊዮን ዶላር ገቢ ማግኘቱን ገልጧል፡፡
“ዘ ዊክንድ” በሚል ቅጽል ስሙ የሚታወቀው የግራሚ ተሸላሚው አቤል፤ ከዘንድሮ የአለማችን ከፍተኛ ተከፋይ 100 ዝነኞች መካከል የ30ኛ ደረጃን መያዙን የጠቆመው ዘገባው፣ “ቢዩቲ ቢሃይንድ ዘ ማድነስ” የተሰኘውና ከ2 ሚሊዮን ኮፒ በላይ የተቸበቸበው የሙዚቃ አልበሙ ለድምጻዊው ከፍተኛ ገቢ ማግኘትና በዝርዝሩ ውስጥ መካተት ትልቅ አስተዋጽኦ ማበርከቱን ገልጧል፡፡
ለ117 አለማቀፍ የሙዚቃ ሽልማቶች በመታጨት፣ ሁለት የግራሚና ስምንት የቢልቦርድ ሽልማቶችን ጨምሮ 36 አለማቀፍና ክልላዊ የሙዚቃ ሽልማቶችን ያገኘውና በወቅቱ የአለማችን የሙዚቃ መድረክ፣ አብሪ ኮከብ ሆኖ የወጣው አቤል፤ ባለፉት 12 ወራት ከአልበም ሽያጭ፣ ከሙዚቃ ኮንሰርቶች፣ ከኩባንያዎች ስምምነትና ከመሳሰሉት በድምሩ 55 ሚሊዮን ዶላር ሰብስቧል፡፡

Monday, 25 July 2016 09:35

የዘላለም ጥግ

(ስለ ታሪክ)

ታሪክ ሊወገዱ የሚችሉ ነገሮች ድምር ውጤት
ነው፡፡
ኮንራድ አድኖር
- ታሪክ ስምምነት ላይ የተደረሰበት ተረት
አይደለምን?
ናፖሊዎን ቦናፓርቴ
- በሁለተኛው የዓለም ጦርነት የምርምርን ፋይዳ
ተገንዝበናል፡፡
አማር ቦሴ
- ትልቁ ጠላቴ ጊዜ ነው፡፡
ኢቪታ ፔሮን
- የሰው ልጅ ታሪክ የሃሳቦች ታሪክ ነው፡፡
ሉጂ ፒራንዴሎ
- የታሪክ ፀሐፊ፡- ያልተሳካለት የረዥም ልብወለድ
ፀሐፊ ነው፡፡
ኤች.ኤል.ሜን
- እግዚአብሔር ያለፈውን ለመለወጥ አይችልም፤
የታሪክ ፀሃፍት ግን ይችላሉ፡፡
ሳሙኤል በትለር
- ታሪክ፤ ማብቂያ የለሽ የተሳሳተ የአኗኗር ዘይቤ
ድግግሞሽ ነው፡፡
ሎውረንስ ዱሬል
- አብዮቶች የታሪክ አሽከርካሪ ሞተሮች ናቸው፡፡
ካርል ማርክስ
- የዘመናዊ መንግስታትን ማህበራዊና ፖለቲካዊ
ታሪክ ለማጥናት ከፈልግህ፣ ስለ ገሃነም አጥና፡፡
ቶማስ ሜርቶን
- የጥበብ ባለሙያ ስራ የዘመኑ ታሪክ እማኝ መሆን
ነው፡፡
ሮበርት ራውስሽንበርግ
- ታሪክ በአጠቃላይ መጥፎ መንግስት እንዴት ያለ
እንደሆነ ብቻ ነው የሚነግረን፡፡
ቶማስ ጄፈርሰን
- የነፃ ሰዎች ታሪክ የሚፃፈው በአጋጣሚ ሳይሆን
በምርጫ ነው፤ በራሳቸው ምርጫ!
ድዋይት ዲ. አይዘንአወር
- ቤተ-መፃህፍት የሃሳቦች ማዋለጃ ክፍል ነው -
ታሪክ ነፍስ የሚዘራበት ሥፍራ፡፡
ኖርማን ኮውሲንስ

በፖሊስ መኮንንነትና በመረጃ ባለሙያነት ሀገራቸውን ያገለገሉትሌተና ኮሎኔል ተፈራ ካሳ “ዘፍ
ያለው” በሚል ርዕስ ያዘጋጁት መፅሃፍ ለገበያ ቀርቧል። ኮለኔሉ በ20 ዓመት አገልግሎታቸው የአይን እማኝ የሆኑበትን የኢትዮ ሶማሌ ጉዳይ እንዲሁም በወቅቱ የነበረውን የአገራችን አጠቃላይ ፖለቲካ ትኩሳት በመረጃ አስደግፈው በትረካ መልክ ያቀረቡበት ይሄው መፅሀፍ
የስለላና የአፈና ትንቅንቅን የሚያስቃኝ እውነተኛ ታሪክ ሲሆን በሁለተኛው ‹‹ለንባብ ለህይወት›› የመፅሀፍት አውደርዕይ መክፈቻ ላይ በድምቀት ተመርቋል፡፡ሌተናል ኮሎኔሉ መፅሐፉን ፅፈው ለህትመት ያዘጋጁት በ1985 ዓ.ም ቢሆንም በተለያዩ ምክንያቶች የህትመት ብርሀን ሳያገኝ እንደቆየ የተገለፀ ሲሆን እርሳቸው ካለፉ በኋላ ልጃቸው ቴዎድሮስ ተፈራ መፅሐፉን የበለጠ በአርትኦት አበልፅጎ ለንባብ እንዳበቃው ለአዲስ አድማስ ገልጿል፡፡ ሌተናል ኮሎኔሉ 12 ዓመት በፖሊስ ሰራዊት ውስጥ በአስተዳደር፣ በወንጀል ምርመራ በቴክኒክ ክፍል ስምንት ዓመት
ደግሞ በፀጥታ ጥበቃ መስሪያ ቤት የመረጃ ሀላፊዎች የቅርብ ረዳት ሆነው ባገለገሉበት ወቅት በአይናቸው ያዩዋቸው የተሳተፉባቸው እውነተኛ ክንውኖች በመፅሀፉ ተካተዋል መፅሀፉ በ341 ገፅ ተመጥኖ በ150 ብር እና በ25 የአሜሪካ ዶላር ለገበያ ቀርቧል፡፡