Administrator

Administrator

በቦብ ላይ የተቃጣውን የግድያ ሙከራ ይተርካል
   በሬጌ ሙዚቃ ንጉሱ በቦብ ማርሊ የህይወት ታሪክ ላይ ተመስርቶ፣ በጃማይካዊው ደራሲ ማርሎን ጄምስ የተጻፈው “ኤ ብሪፍ ሂስትሪ ኦፍ ሰቨን ኪሊንግስ” የተሰኘ የልቦለድ መጽሃፍ “ማን ቡከር ፕራይዝ” የተባለውን አለማቀፍ ሽልማት እንዳገኘ ቢቢሲ ዘገበ፡፡
በ44 አመቱ ጃማይካዊ ደራሲ ማርሎን ጄምስ የተጻፈው መጽሃፉ፤ እ.ኤ.አ በ1970ዎቹ በቦብ ማርሊ ላይ የተቃጣ የግድያ ሙከራን መሰረት አድርጎ እንደተተረከ የጠቆመው ዘገባው፣ በወቅቱ በጃማይካ ስር ሰድዶ የነበረውን የፖለቲካ ሙስና እንደሚዳስስም ገልጧል፡፡
686 ገጾች ያሉት መጽሃፉ፣ ቦብ ማርሊ እ.ኤ.አ በ1976 በአገሪቱ መዲና ኪንግስተን በተዘጋጀ የሙዚቃ ኮንሰርት ላይ የአገሪቱን የፖለቲካ ውጥረት ለማርገብ ሲል፣ ሙዚቃውን ለመጫወት ባሰበበት ወቅት የተደራጁ ወንጀለኞች በመኖሪያ ቤቱ ላይ ተኩስ እንደከፈቱና ድምጻዊው ለጥቂት ከሞት እንደተረፈ ይተርካል፡፡
ይህን ሽልማት በማግኘት የመጀመሪያው ጃማይካዊ የሆነው ደራሲው፣ ለህትመት ያበቃው ሶስተኛ መጽሃፉ በሆነው በዚህ ስራው 50 ሺህ ፓውንድ እና ዋንጫ እንደተሸለመ የተገለጸ ሲሆን፣ ደራሲው በአሁኑ ወቅት በአሜሪካ ሚኒሶታ ግዛት የፈጠራ ጽሁፍ መምህር ሆኖ እየሰራ እንደሚገኝ ተነግሯል፡፡

    - ከግማሽ በላይ የሚሆነው የአለማችንን ሃብት የተያዘው፣ ከህዝቡ 1 በመቶ በሚሆኑ ባለጠጎች ነው
           - ግማሹ ድሃ የአለም ህዝብ፣ ከአለማችን ሃብት 1 በመቶ ብቻ ይደርሰዋል
  በያዝነው የፈረንጆች አመት 2015 ከግማሽ በላይ የሚሆነው የአለማችን ሃብት፣ ከአጠቃላዩ የአለም ህዝብ 1 በመቶ ያህል ብቻ በሚሆኑ የተለያዩ አገራት ባለጠጎች እጅ ውስጥ እንደሚገኝና በከፋ ድህነት ውስጥ የሚገኘው ግማሹ የአለማችን ህዝብ ከአጠቃላዩ የአለም ሃብት 1 በመቶውን ብቻ እንደያዘ በጥናት መረጋገጡን ዘ ኢንዲፔንደንት ከትናንት በስቲያ ዘገበ፡፡ክሬዲት ሲዩሴ የተባለው ተቋም በ200 የተለያዩ የዓለማችን አገራት ዙሪያ የሰራውንና ባለፈው ማክሰኞ ይፋ ያደረገውን አለማቀፍ የሃብት ስርጭት አመታዊ ሪፖርት ጠቅሶ ዘገባው እንዳለው፣ ከአለማችን አገራት መካከለኛ ገቢ የሚያገኙ በርካታ ዜጎች ያሏት ቀዳሚዋ አገር ቻይና ሆናለች፡፡ከአለማችን ህዝብ 14 በመቶ የሚሆነው ወይም 664 ሚሊዮን ያህሉ፣ መካከለኛ ገቢ እንደሚያገኝ የጠቆመው ጥናቱ፣ 109 ሚሊዮን ያህል መካከለኛ ገቢ የሚያገኙ ዜጎች ያሏት ቻይና፣ አምና ቀዳሚ የነበረችውንና ዘንድሮ 92 ሚሊዮን መካከለኛ ገቢ የሚያገኙ ዜጎች እንዳሏት የተረጋገጠውን አሜሪካ ቀድማ የመጀመሪያውን ስፍራ መያዟን ገልጧል፡፡
እስካለፈው ግንቦት በነበሩት 12 ወራት በአለማችን የሃብት ክፍፍል ረገድ የሚታየው ክፍተት ክፉኛ መባባሱን የገለጸው የተቋሙ ሪፖርት፣ ከአለማችን ህዝብ 71 በመቶው ከ10 ሺህ ዶላር በታች፣ 21 በመቶው ከ10ሺህ እስከ 100 ሺህ ዶላር፣ 7.4 በመቶው ከ100 ሺህ እስከ  1 ሚሊዮን ዶላር፣ ቀሪው 0.7 በመቶ ህዝብ ደግሞ ከ1 ሚሊዮን ዶላር በላይ ሃብት አለው ብሏል፡፡
የአለማችን አጠቃላይ ሃብት አምና ከነበረበት የ12.4 ትሪሊዮን ዶላር ቅናሽ በማሳየት፣ ዘንድሮ 250 ትሪሊዮን ዶላር ደርሷል ያለው ሪፖርቱ፣ ከዚህ ሃብት 16 በመቶውን የያዘችው ቻይና ስትሆን፣ አሜሪካ በ12 በመቶ፣ እንግሊዝ ደግሞ 4 በመቶውን ይዘዋል ብሏል፡፡

Saturday, 17 October 2015 08:52

ኢፕሊፕሲ - የሚጥል በሽታ

• በዓለማችን ከ50 ሚሊዮን በላይ የኢፕሊፕሲ ተጠቂዎች አሉ
• ከነዚህ መካከል 1 ሚሊዮን የሚሆኑት በአገራችን ይገኛሉ
• ከህሙማኑ መካከል 85% የሚሆኑት ህክምና አያገኙም

    በአገረ እንግሊዝ ለሃያ አምስት አመታት ቆይታ ወደ አገሯ በተመለሰችውና የኢፕሊፕሲ (የሚጥል በሽታ) ታማሚ በነበረችው ወ/ሮ እናት የእውነቱ የተቋቋመው Care Epilepsy Ethiopia ህብረተሰቡ ስለበሽታው ያለውን ግንዛቤ ለማሳደግና በህሙማኑ ላይ የሚደርሰውን የአድልኦና የመገለል ችግር ለማስወገድ የሚያስችል የግንዛቤ ማስጨበጫ ፕሮግራም ሰሞኑን በጁፒተር ሆቴል አካሂዶ ነበር፡፡ በእለቱም በሽታው በአሁኑ ወቅት በአለም አቀፍ ደረጃ ያለበትን ሁኔታና እንዲሁም በአገራችን ያሉ የበሽታው ተጠቂዎች ቁጥርና የሚደርስባቸወን ስቃይ ለማሳየት ተሞክሯል፡፡ በሽታው ጊዜና ቦታን ሳይመርጥ በማንኛውም ሁኔታ ታማሚውን ስለሚጥለው ህሙማኑ አሳት ላይ በመውደቅ፣ ከፎቅ ላይ በመከስከስና መሰል አደጋዎች ገጥመዋቸው በአሰቃቂ ሁኔታ ጉዳት እንደደረሰባቸው የሚያሳዩ የተለያዩ ፎቶግራፎችም ለፕሮግራሙ ታዳሚዎች ቀርበዋል፡፡የኬር ኢፕሊፕሲ ኢትዮጵያ መስራችንና ስራ አስኪያጅ ወ/ሮ እናት የእውነቱ፤ ድርጅቱን ለማቋቋም ያነሳሳቸውን ነገር አስመልክተው ሲናገሩ፤ በኢፕሊፕሲ በሽታ ተይዤ ለአመታት ስሰቃይ ብቆይም እድለኛ ሆኜ ጥሩ ህክምና በሚሰጥበት አገር በመኖሬ ምክንያት ህክምናውን አግኝቼ ከበሽታዬ ለመዳንና በህይወቴ የምፈልገውን ለመሆን ችያለሁ፡፡ በአሁኑ ወቅት በፐብሊክ ሄልዝ ስፔሻላይዝድ አድርጌአለሁ፡፡ ማስተርሴንም ያገኘሁት በዚሁ ነው፡፡ ይህንን እድል ሳያኙ ቀርተው በበሽታው የተያዙና እጅግ የከፋ ስቃይና እንግልት የሚደርስባቸወ ኢትዮጵያዊ እህት ወንድሞቼ ግን መድሃኒትና ህክምና እንኳን ለማግኘት ሳይችሉ ቀርተዋል፡፡ ከዚህ በከፋ ሁኔታ ደግሞ በህብረተሰቡ የመገለል ሁኔታ ይደርስባቸዋል፡፡ ስለዚህም ይህንን ነገር ለመቀየርና በበሽታው የሚሰቃዩ እህትና
ወንድሞቼን ለመርዳት፣ ህክምናውን ለማግኘት የሚችሉበትን ሁኔታ ለማመቻቸት፣ ህብረተሰቡም በበሽታው ላይ ያለውን አመለካከት ቀይሮ ለህሙማኑ ተገቢውን ፍቅርና እንክብካቤ እንዲሰጣቸው ለማድረግ በማሰብ ድርጅቱን አቋቁመናል፡፡ ከተቋቋመ ቅርብ ጊዜ ቢሆንም በዚህ ዙሪያ በርካታ
የግንዛቤ ማስጨበጫ ስራዎችን ስንሰራ ቆይተናል፡፡ አሁን ደግሞ የበለጠ ወደ ህዝቡ ውስጥ ለመግባትና በሽታው በህሙማኑ ላይ እያደረሰ ያለውን ችግር ለማስወገድ ጥረት በማድረግ ላይ ነን ብለዋል፡፡
የሮማውን ገዡ ጁሊየስ ቄሳርን፣ የመቄዶኒያውን ንጉስ ታላቁ እስክንድርንና የፈረንሳዩን የጦር መሪ ናፖሊዮን ቦናፓርት ሲያሰቃይ የኖረው ኢፕሊፕሲ፤ በተወሰኑ የአንጐል ነርቭ ሴሎች ውስጥ በሚከሰት ጊዜያዊ የኤሌክትሪክ ንዝረት ሳቢያ የሚፈጠርና አንጐል ለአጭር ጊዜ የወትሮ ስራውን እንዳይሰራ የሚያደርግ በሽታ ነው፡፡ ሁለት ዋና ዋና የኢፕሊፕሲ አይነቶች እንዳሉና Generalized እና focul በሚል ስያሜ እንደሚጠሩ ባለሙያዎች ይናገራሉ፡፡ Generalized የምንለው የኢፕሊፕሲ አይነት ታማሚውን መሬት ላይ የሚጥል፣ የሚያንቀጠቅጥና ሰውነትን የሚያግተረትር ሲሆን Focul የሚባለው ደግሞ በዝምታ በመዋጥ፣ ለጥቂት ሰከንዶች አካባቢንና ራስን በመሳት የሚገለፅ ህመም ነው፡፡ በሽታው ከሰው ወደ ሰው የመተላለፍ ባህርይ የለውም፡፡ ህብረተሰቡ በሽታው ከሰው ወደ ሰው እንደሚተላለፍ ስለሚያምን፣ ብዙውን ጊዜ የበሽታው ተጠቂዎች ራሳቸውን ስተው በማወድቁበት ጊዜ ለመርዳትና ጉዳት እንዳይደርስባቸው ለማድረግ ፍርሃት ያድርበታል፡፡ የውስጥ ደዌ ህክምና እና የነርቭ ህክምና ስፔሻሊስቷ ዶክተር ሞህላ ዘበንጉስ ይህንኑ ጉዳይ አስመልክተው ሲናገሩ፤ “ኢፕሊፕሲ በተለያዩ ምክንያቶችና መነሻዎች ሳቢያ
በአንጐላችን ነርቮች ውስጥ በሚከሰት ድንገተኛና ጊዜያዊ የኤሌክትሪክ ንዝረት ምክንያት የሚፈጠር በሽታ ሲሆን ከታማሚ ወደ ጤነኛ ሰው በንኪኪ፣ በትንፋሽና መሰል ሁኔታዎች ፈፅሞ የማይተላለፍ
ነው፡፡ ለበሽታው መነሻ ምክንያቶች ይሆናሉ ተብለው ከሚታሰቡ ነገሮች መካከል በወሊድ ወቅት ከአስቸጋሪ ምጥ ጋር ተያይዞ በአንጐል ላይ የሚሰት አደጋ፣ የአንጐል ኢንፌክሽን፣ አንጐል ውስጥ
የሚያድጉ እጢዎች፣ በጭንቅላት ላይ የሚደርሱ የተለያዩ ጉዳቶች፣ ስትሮክና የደም ውስጥ የስኳር
መጠን በጣም ዝቅ ማለት ጥቂቶቹ ናቸው፡፡ በአገራችን በሽታው ወደ አንድ ሚሊዮን በሚጠጉ ሰዎች ላይ የሚታይ ሲሆን ከእነዚህ ህሙማን መካከል ህክምናውን የሚያኙት ከ5-10 በመቶ የሚሆኑት ብቻ ናቸው ብለዋል፡፡ በሽታው በህፃናትና በእድሜ በገፉ ሰዎች ላይ በስፋት እንደሚታይም ሃኪሟ ተናግረዋል፡፡
የኢፕሊፕሲ በሽታን 70% በመድሃኒት መቆጣጠር እንደሚቻል የሚገልፁት ዶክተር ምህላ፤ ታማሚዎች ህክምናውን በአግባቡ ከተከታተሉት በሽታውን ተቆጣጥረው መደበኛ ህይወት ለመምራት እንደሚችሉና በሽታው እንደ ስኳር፣ ደም ግፊት ህመም የሃኪም የቅርብ ክትትል የሚያስፈልገው ተናግረዋል፡፡ህክምናው በሽተኛው እንዴት እንደሚያደርገው መረጃ ከተሰበሰበ በኋላ በምልክቶቹ ተለይቶ ለሚታወቀው በሽታ መድሃኒት በመስጠት ምክንያታቸው የሚታወቁትን የኢፕሊፕሲ በሽታ ለመንስኤው ምክንያት የሆነውን ነገር ነጥሎ በማውጣትና በማከም ለመከላከል እንደሚቻልም ሀኪሟ ገልፀዋል፡፡ ህክምናው ረዘም ያለ ጊዜን የሚወስድ ሲሆን የጭንቃላትን ኤሌክትሪክ ንዝረት በሚለኩ መሳሪያዎች በመለካት ህመሙ ያለበትን ደረጃ በመከታተል፣ ታማሚው መድሃኒቱን በአግባቡ እንዲወስድና ከህመሙ ነፃ በሚሆን ጊዜ መድሃኒቱን እንዲያቆም በማድረግ፣ ጤናማና ሰላማዊ ህይወት እንዲመራ ማድረግ መቻሉንም ሃኪሟ አስገንዝበዋል፡፡
ኢፕሊፕሲ (የሚጥል በሽታ) በህክምና ቁጥጥር ስር እስካልዋለ ድረስ ምን ጊዜና የት ቦታ ህመምተኛውን እንደሚጥለው ማወቅ ስለማይቻል ከፍተኛ ጥንቃቄ ማድረግ ይገባል፡፡ የእሳት፣ የመብራት ወይንም የቴሌቭዥን ማንፀባረቅና ማብለጭለጭ በሽታውን ሊቀሰቅሰው እንደሚችል አንዳንድ መረጃዎች ይጠቁማሉ፡፡ በሽታው ድንገት የሚቀሰቀስና ታማሚውን እጅግ ለከፋ አደጋ የሚዳርግ በመሆኑ የሚጥል በሽታ ያለባቸው ሰዎች መኪና ከማሽከርከር፣ ሳይክል ከመንዳት፣ ከዋና፣ ፈረስና በቅሎ ከመጋለብ፣ ከፍታ ቦታዎች ላይ ከመስራትና እንደ አልኮልና ጫት ካሉ ሱሶች በእጅጉ መቆጠብ እንደሚኖርባቸው ዶክተር ምእላ አስገንዝበዋል፡፡   

ኖር በዪ የኹጅር የጋኸምን ምስ) - የቤተ ጉራጌ ተረት

ከዕለታት አንድ ቀን ሁለት ጓደኛሞች፤ ገንዘብ በጣም ይቸግራቸውና በምን መንገድ ራታቸውን እንደሚበሉ ያስባሉ፡፡
አንደኛው -  ከሱቅ ገንዘብ እንበደርና የፈለግነውን ምግብ እንብላ
ሁለተኛው - ለባለሱቁ ባለፈው ያለብንን ዕዳ ስላልከፈልነው ምርር ብሎታል፡፡ “ያንን
ካልመለሳችሁልኝ ሁለተኛ ዐይናችሁን አላይም” ብሎኛል፡፡
አንደኛው -  እሺ ሌላ ዘዴ አንተ አምጣ
ሁለተኛው - አጐቴን ሄጄ ላስቸግረዋ?
አንደኛው -  የእራት ስጠን ልትለው ነው? የሆነ ሰበብ ያስፈልግሃልኮ?
ሁለተኛው - የቤት ኪራይ አነሰኝ ሙላልኝ ልበለው?
አንደኛው - አሞሃል? ነገ የሚጣራ ነገር ዛሬ ዋሽተህ የወደፊት እንጀራ ገመድህን በትንሽ ነገር ልትበጥስ ነው?
ሁለተኛው - ታዲያ ምን ማድረግ ይሻለናል?
አንደኛው - አንድ ዘዴ ታየኝ
ሁለተኛው - ምን?
አንደኛው - እዚህ ሠፈር አንድ ድንኳን ተጥሏል፡፡ የሆነ ሰውዬ ሞቷል፡፡ ለምን ራት ሰዓት
አካባቢ እዛ ሄደን፤ መቼም እራት ማቅረባቸው አይቀርምና፤ ቁጭ ብለን   
አንጠብቅም?
ሁለተኛው - አሁን አሪፍ ዘዴ ዘየድክ
አንደኛው - በቃ እዛ እንሄዳለን!
ተያይዘው ወደ ልቅሶው ድንኳን ሄዱ፡፡ ገቡ፡፡
ጠበቁ፡፡ ጠበቁ፡፡ ጠበቁ፡፡ ራት አልመጣም፡፡
12 ሰዓት ተኩል፡፡ አንድ ሰዓት፡፡ ሁለት ሰዓት፡፡ ራት፤ የለም፡፡ ግራ ገባቸው፡፡
አንደኛው - ራት ይቀርባል? አይቀርብም? ለምን አንጠይቅም?
ሁለተኛው - ይሻላል፡፡ ግን ማንን እንጠይቅ?
አንደኛው - እዛ ጋ ወዲህ ወዲያ የሚሉትን ሰውዬ እንጠይቃቸው፡፡
ሁለተኛው - እሺ
አንደኛው ፤ ወደተባሉት ሰው ጠጋ ይልና፤
“እንዴት ነው፣ ራት አይቀርብም እንዴ?”
ሰውዬው - አይ ልጆቼ! ሟቹ ሰውዬ ራሱ የሞተው ርቦት ነው!  
***
ድህነታችንን መጋራት እንጂ መታገል ካቃተን መንገዳችን በእንቅፋት የተሞላ እንደሚሆን ሳይታለም የተፈታ ነው፡፡ ከሥሩ ለመንቀል ሥር-ነቀል እርምጃ ያስፈልጋል፡፡ ይህን ለማድረግ ደግሞ ሥር - ነቀል አስተሳሰብ ማዳበር ያስፈልጋል፡፡ ለዚህ የምሁራንና ባለሙያዎች አስተሳሰብ መዳበርና የፈቃደ ልቦናቸው መኖር ወሳኝ ነው! በሀገራችን ለምሁራንና ለባለሙያዎች የምንሰጠው ትኩረትና ክብር አናሳ ነው ቢባል ማጋነን አይሆንም፡፡ ድህነትን ለመቀነስ መወሰድ ካለባቸው ዓይነተኛ እርምጃዎች አንዱ ይኸው ለምሁርና ለባለሙያ የምንሰጠው ትኩረት ነው! ምሁራኑም ለሀገራቸው የሚሰጡት ትኩረት ከጥቅም የዘለለ መሆን ይኖርበታል፡፡ የጊዜው ነገር ሆኖ ነው እንጂ ይሄን አይስቱትም! ሹማምንት የህዝብ ፍቅር ሊኖራቸው ይገባል፡፡ ከህዝብ ጋር መኖር፣ ህዝብ መሀል መኖር አለባቸው፡-
“ዓለም አደገኛ ናት ጠላቶችም በየቦታው አሉ፡፡ ሁሉሰው ራሱን መጠበቅ አለበት፡፡ ምሽግ የመጨረሻ መጠበቂያ ቦታ ይመስለናል፡፡ ከሰው ተነጥሎ መቀመጥ ግን ለበለጠ አደጋ ያጋልጣል፡፡ ከአስፈላጊ መረጃ ያናጥባል፡፡ በግልፅ እንድንታይና ቀላል ኢላማ ያደርገናል፡፡ ስለዚህ ከህዝብ መካከል ሆኖ፣ ወዳጅ እየፈጠሩ መዋሃዱ ይመረጣል፡፡ ከጠላቶች ጥቃት ጋሻ የሚሆንህ ጀማው ነው” ይላል ሮበርት ግሪን፡፡ በተግባር የመፈተኛው ሰዓት አሁን ነው፡፡ ለራስ ጥቅም ከማሰብ ለሀገር ማሰብ ልዩነቱ የሚረጋገጠው ልባችን፣ አፋችንና ተግባራችን አንድ ሲሆኑ ነው፡፡ መለኪያው ከህዝብ ጋር መሆን ነው፡፡ እንደህዝብ ማሰብ ነው፡፡ “ሸክላ ሲሰበር ገል ይሆናል፡፡ መኳንንትም ሲሻሩ ህዝብ ናቸው” የሚለውን ማስተዋል ዋና ነገር ነው፡፡ አዲስ የተሾሙ ሰዎቻችንን ልቦና ህዝባዊነት አይንሳቸው፡፡ ሀገራዊነት አይንሳቸው!
የተሻለ፣ ከትላንት የተለየ ነገር እንዲኖር እንመኝ፡፡ የምናውቃቸው ሰዎች የምናውቀውን ነገር የሚደግሙልን ከሆነ መቀየራቸው ትርጉም ያጣል! አብረን እናስብ! ምሁራንን እናማክር! ለሀገር አሳቢዎች እኛ ብቻ ስላልሆንን ከማህበረሰቡ የረባ አዕምሮና አብራሄ ህሊና (Enlightenment) ያላቸውን ሰዎች የመቀላቀል የተባና ሩህሩህ ልቦና ይኑረን! ይህን ተሐድሶ ያልተላበሱ ሰዎች ይዘን ብዙ አንጓዝም! ይህ ካልሆነ “ኖር በይው ልብሱን፣ ሰውዬውስ የቅድሙ ነው” የሚለው ተረት ዕውን ይሆናልና እንጠንቀቅ!  

 በደራሲ አሳየ ደረበ የተጻፈው “እስኪነጋ ድረስ” የተሰኘ የወጎች፣ የአጫጭር ልቦለዶችና የግጥሞች ስብስብ መጽሃፍ ሰሞኑን በገበያ ላይ መዋሉን ደራሲው በተለይ ለአዲስ አድማስ ገለጸ፡፡
በተለየ አቀራረብ የተሰናዳው መጽሃፉ፤በተለያዩ ማህበራዊ ጉዳዮች ዙሪያ የሚያጠነጥኑ 18 ያህል ወጎችንና አጫጭር ልቦለዶችን የያዘ ሲሆን በታሪኮቹ መካከልም ከታሪኮቹ ሃሳቦች ጋር ተያያዥ የሆኑ 30 ያህል ግጥሞችን አካትቷል፡፡
ደራሲው ለህትመት ያበቃው የመጀመሪያ ስራው የሆነው “እስኪነጋ ድረስ”፤ በአዲስ አበባ እና በክልል ከተሞች በሚገኙ የመጽሃፍት መደብሮችና አዟሪዎች ዘንድ በ50 ብር እየተሸጠ ይገኛል፡፡
ደራሲ አሳየ ደረበ በፌስቡክ ማህበራዊ ድረ-ገጽ አዝናኝና አስተማሪ ወጎችን፣ የግል እይታዎችን፣ ግጥሞችንና የተለያዩ ጽሁፎችን በስፋት በማቅረብና በርካታ አንባብያንና ተከታዮችን በማፍራት የሚታወቅ ሲሆን በቀጣይም ሌሎች የወጎችና የአጫጭር ልቦለድ መጽሃፍትን ለአንባብያን የማድረስ ዕቅድ እንዳለው ለአዲስ አድማስ ተናግሯል፡፡

ኤፍሬም አርት ስቱዲዮና ጋለሪ የሰዓሊ ናኦድ ክፍሉ በርካታ የስዕል ስራዎች የተካተቱበትን “ትውስታ” የተሰኘ የስዕል አውደ ርዕይ ከትላንት በስቲያ ከቀኑ 11፡30 ጀምሮ በብሄራዊ ሙዚየም ለእይታ አበቃ፡፡“ትውስታ” የስዕል አውደ ርዕይ ኢትዮጵያ ውስጥ የነበሩ የቀድሞ ባቡሮችን ወደ ሃሳብ ቀይሮ የሳለበትና ሌሎች 48 ያህል ስዕሎች የቀረቡበት እንደሆነ የኤፍሬም አርት ስቱዲዮና ጋለሪ ባለቤት አቶ ኤፍሬም ለሚ ተናግረዋል፡፡ ሰዓሊው ከዚህ ቀደም ከሌሎች ሰዓሊያን ጋር በቡድን ለበርካታ ጊዜያት ስራዎቹን ለእይታ ማቅረቡን የገለፁት አቶ ኤፍሬም፤ “ትውስታ” በግሉ ያቀረበው የመጀመሪያው አውደ-ርዕይ መሆኑን ገልፀዋል፡፡ኤፍሬም አርት ስቱዲዮና ጋለሪ ከዚህ በፊት ሦስት የቡድን አውደርዕዮችን ለተመልካች ያቀረበ ሲሆን የአንድ ሰዓሊ ስራዎችን ለብቻ ሲያቀርብ የአሁኑ የመጀመሪያው መሆኑን የጋለሪው ባለቤት ተናግረዋል፡፡ አውደ ርዕዩ እስከ ጥቅምት 3 ቀን 2008 ዓ.ም ለተመልካች ክፍት ሆኖ እንደሚቆይም ታውቋል፡፡

 ማህበረ ቅዱሳን፤ በአቡነ ጐርጐሪዎስ የዜማ መሳሪያዎች ትምህርትና ስልጠና ማዕከል ባለፈው ዓመት ያሰለጠናቸውን ተማሪዎች፤ ዛሬ ከቀኑ 7፡30 ሰዓት ጀምሮ በማህበሩ ህንፃ ላይ በሚገኘው አዳራሽ እንደሚያስመርቅ አስታወቀ፡፡ማህበሩ ዘንድሮ ለ11ኛ ጊዜ የሚያስመርቃቸው 300 ተማሪዎችን እንደሆነ ተገልጿል፡፡ ተመራቂዎቹ በስልጠና ቆይታቸው በበገና፣ በመሰንቆ፣ በልሳነ-ግዕዝ እና በከበሮ አመታት ትምህርት ማግኘታቸውን የጠቆመው ማህበሩ፤ የምረቃ ሥነስርዓቱ ሊቃነ ጳጳሳት፣ ሊቃውንተ ቤተ-ክርስቲያን፣ መንግሥታዊና መንግሥታዊ ያልሆኑ ድርጅቶች ተወካዮችና ታዋቂ ግለሰቦች በተገኙበት ይከናወናል ተብሏል፡፡

    የእርሻና ግብርና ጥምር ተመራማሪው አቶ ደቻሳ ጅሩ ከሳምንት በፊት በቀረበው ቃለምልልስ በአትሌቲክስ የቡድን ስራን ከወፎች በረራ መማር እንደሚቻል በምሳሌነት አንስተው ያደረጉትን ምርምር አብራርተዋል፡፡ በተጨማሪም የአየር ሁኔታና የቦታ ተስማማሚነት በተመለከተ አጭር ገለፃም ነበራቸው፡፡  በዓለም አቀፍ ውድድሮች የኢትዮጵያ አትሌቶች በሚኖራቸው  ውጤታማነት የአየር ሁኔታን በሳይንሳዊ መረጃዎች አገናዝቦ ስልጠና እና ዝግጅት ማድረግ ወሳኝ መሆኑን አስገንዝበዋል፡፡ አቶ ደቻሳ ጅሩ ከስፖርት አድማስ ያደረጉት ሰፊ ቃለምምልስ እነሆ በ3ኛ ክፍል ይቀጥላል፡፡ አትሌቲክስ ከፆታ፤ አለባበስ፣ ቀለማት፤ ቁመትና ክብደት አንፃር ምርምሮቻቸውን በመጠቃቀስ ያስረዳሉ፡፡
ባለፉት ሁለት የዓለም ሻምፒዮና እና የኦሎምፒክ መድረኮች ላይ የኢትዮጵያ ቡድን ወንድ አትሌቶች ብዙም ስኬታማ አልነበሩም ማለት ይቻላል፡፡ ሴቶቹ ግን  የተሻሻለ ውጤት እያስመዘገቡ ናቸው፡፡ ልዩነቱ ከምን እንደመጣ ብዙ ግልፅ አይደለም፡፡ ለመሆኑ አትሌቲክስ  ከፆታ እና ሌሎች ተያያዥ ሁኔታዎች አንፃር እንዴት ይመለከቱታል?
በአትሌቲክስ ስፖርት ውጤታማነት የሚገኘው የፆታ ሁኔታዎችን በሳይንሳዊ ምርምሮች አገናዝቦ በሚሠራ መዋቅር ነው፡፡ የፆታ ልዩነት በስልጠና እና በማንኛውም የውድድር ዝግጅቶች የሚኖረው ተፅእኖ  በትኩረት የምንሰራበት አቅጣጫ መሆን አለበት፡፡  ወንድ ቅዝቃዜ ይስማማዋል፤ ሴት በሙቀት ውጤታማ ትሆናለች፡፡ ለምን? የስነተፈጥሮ ጉዳይ ነው፡፡ ቀነኒሳና ጥሩነሸ በ3000 ሜትር ከፍታ አድገዋል፡፡ ተመሳሳይ ውሃና አየር ጠጥተው እና ተንፍሰው ወደ አለም አትሌቲክስ የውጤት  ማማ ወጥተዋል፡፡  በ2007 እ.ኤ.አ በኬንያዋ የባህር ጠረፍ ከተማ ሞምባሳ የዓለም አገር አቋራጭ ሻምፒዮና መደረጉን ታስታውሳለህ፡፡ በዚያ ሻምፒዮና ላይ የኢትዮጵያ ቡድን በነበረው ተሳትፎና ያልተጠበቀ ውጤት በምሳሌነት ላነሳልህ ነው፡፡ በሴቶች ምድብ በረጅም ርቀት ጥሩነሽ ዲባባ 2ኛ መሆኗ ትልቁ ውጤት ነበር፡፡ ሌሎች ሴት አትሌቶች  ደግሞ 3ኛና 4ኛ ደረጃዎችን አሳክተዋል፡፡ በአንፃሩ በወንዶቹ ምድብ ግን አትሌቶቻችን እስከነጭራሹ እንዳልነበሩ ሆነዋል፡፡ ወንዶቹ ያልተሳካላቸው በብቃት ማነስ አልነበረም፡፡ የፆታ ልዩነት የፈጠረው እድል ነው፡፡ ከተፈጥሮ አኳያ የአየር ምቾት በፆታዎች መካከል ተጽዕኖ ይኖረዋል፡፡ ለወንድ ቅዝቃዜ ስለሚስማማው ለሴት ሙቀት ፋይዳ ስለሚሆን ነው፡፡ በሌላ በኩል ሞምባሳ ላይ የኤርትራው ዘረሰናይ በወንዶች 1ኛ መውጣቱ የሚጠቀስ ነው፡፡ ዘረሰናይ ከሞምባሳ ጋር ተመሳሳይ በሆነ የአየር ሁኔታ  ባላት የምጽዋ ከተማ ዝግጅቱን በመስራቱ የተሻለ ብቃት ፈጥሮለታል፡፡ የምፅዋ አየር ከሞምባሳው ጋር መወራረሱ እና ጠንካራ ከሚባሉት አትሌቶች አንዱ ስለበር ብልጫ አሳይቶ አሸንፏል፡፡
የወንድና ሴት መሰረታዊ ልዩነቱ ከስነተዋልዶ አካል አፈጣጠር ይጀምራል፡፡ የወንድ ዘር መራቢያ 37.6 ድ.ሴ. ከሚሞቅ ሰውነት ወጣ ያደረገውና የሽፋን ቆዳውን ‹‹እንደ ቮልስ ራዲያቶር››  ቆዳውን የሸበበው ያለምክንያት አይደለም፡፡ በውስን ዘር ፍሬ ቦታ ላይ የንፋስ(ማቀዝቀዣ) ቦታውን አብዝቶ) አስፍቶ በንፋስ እንዲቀዘቅዝ ነው፡፡ ስለዚህ ወንድ በተፈጥሮ እንደደጋ በግ ሙቀት አይችልም፡ በተቃራኒ ልክ እንደጾታዋ የሴትዋ እንቁላል በሙቀት ውስጥ/ሰውነትዋ ውስጥ/ ስለሆነ ሙቀት(እንፋሎትም) ትችላለች፡፡ ንፋስና ብርድ ግን አትችልም፡፡
ሁኔታውን በደንብ ለመረዳት እንዲያስችል ከምርምሮችዎ ሌላ የሚጠቅሱት የለም…?
አንድ ገጠመኝ ነበረኝ፡፡  የግብርና ምርምር ኢንስትቲውት በየዓመቱ የአለም ሴቶች ቀን ሲከበር ይጋብዘኛል፡፡  አንዲት ታጋይ የነበረች ኮለኔል ለታይ የምትባል ሴት የትግል ተመክሮዋን በመድረክ ስትገልፅ ታዳሚ ነበርኩ፡፡ ጥያቄዎች የማንሳት እድሉን አግኝቼ ነበር፡፡ ከበረሃ እስከጉና ተራራ ባለው የትግል ወቅት ከወንድና ከሴት ማን በብርድ ተሰቃየ፤ በሙቀትስ? የሚል፡፡ ታጋይዋ በሚሰጡኝ ምላሽ  አትሌቲክስን በተመለከተ ላደረግኩት ሳይንሳዊ ጥናት አንድ  ተጨባጭ ፋይዳ ስለሚኖረው በደንብ ይታሰብበት አልኩ፡፡ ኮለኔል ለታይ ማብራርያቸውን ሲቀጥሉ ታጋዮች ባንድ ወቅት ወደ አሰብ መደራሻ የሚገኝ አካባቢ ላይ በደርግ ሰራዊት ተከበው ከውሃ ተቁዋርጠው በጥም እንዲሰው ተደረገ፡፡ መጨረሻ አንድ ወሳኝ ወንድ ታጋይ ሊሰዋ ሲል ጉሮሮውን አርሶ ትንሽ እድሜውን ለሰአታት ለማስረዘም ሽንት ቢፈለግ ጠፋ፡፡ መጨረሻ ከአንድ ሴት ተገኝቶ ወሳኝ ታጋያቸው ነፍስ ሲዘራ የታገዩ ሞራል ነፍስ ዘርቶ መልሰው ውሃውን ተቆጣጠርን በማለት አስገራሚውን የትግል ታሪክ አወጉ፡፡ እጅግ በመደነቅ አዳመጥኳቸው፡፡ ለሳይንሳዊ ግንዛቤ የሚረዳ ገጠመኝ ነበር፡፡ ኮለኔል ለታይንና ታሪኩን በምንጭነት ጠቅሸ ወደፊት በሚታተመው የአትሌትክስ መፅሃፌ በዝርዝር የማብራራው ይሆናል፡፡
የአየር ተስማሚነት ከአለባበስ እና ቀለማትም ጋር ይያዛል?
አለባበስ እና ቀለማት ከሚያመቻቸው ተፈጥሯዊ ሁኔታዎች አንፃር በአጭሩ ላስረዳህ እችላለሁ፡፡ የሽፋን ቀለም እንደአየሩ ሁኔታ መለዋወጥ ተገቢ ነው፡፡ በቁርና ደጋ የምትኖር ንብ መልኳ ጥቁር ነው፡፡ ጥቁር ቀለም ሙቀት ሰብሳቢ ነውና፡፡ ወደ ወይና ደጋ ስንወርድ የንቧ ቀለም በከፊል እየፈጋ፤  ሞቃት ወይም በረሃ ሲሆን ነጭ እየሆነ ይመጣል፡፡ ለፍየሉም ለበጉ እንዲሁ ተመሳሳይ ሁኔታ ነው ያለው፡፡ ከዚህ በመነሳት  ጥቁር ሰዎች ለምን አልነጣንም ብለው ቢጠይቁ ምላሽ የሚሆነው ሰዎች በተፈጥሯችን ተንቀሳቃሽ በመሆናችን ነው፡፡ እንደአየሩ ሁኔታ እንደእስስት መለዋወጥ የልብንም ነው፡፡  ብርዱንም መቀቱንም አስቀድመን በምናስብበት የመከላከል ግንዛቤ ስለምንኖር ነው፡፡ በተለይ ልብስ ስለምንለብስና ስለምንቀያይር እንደ አየሩ ሁኔታ ቀለሙንና የልብሱን ይዘት መወሰን እንችላለን፡፡ ጥቁሩን ጸጉር ሴቶች ከወንዶች በላይ አሳድገው ማጅራታቸው ላይ ማስተኛት ሌላው የመረመርኩት ሁኔታ ነው፡፡ በልምድና በሳይንሳዊ እውቀትም ብንለካው ለኔ የጠለቀና የዘለቀ ሳይንሳዊ ግንዛቤ ነው፡፡ የባህር ሃይል ዩኒፎርም ልብስ መንጣትም እንዲሁ፡፡ በእኔ በኩል  የእርሻ፤ የደንና ዱር እንስሳት ባለሙያ በመሆኔ እነዚህን ሳይንሳዊ ሁኔታዎች ብዙ ምርምሮች አድርጌባቸዋለሁ፡፡ በበግ የምሰራውን የአየር ምቾት ምርምር እንደየፆታው ወደ  አትሌቶች እያወራረስኩ እየተረጐምኩ ሲሆን  መረጃውን በመቀመርም ምርምሩን እየሰራሁ እገኛለሁ፡፡ በመጽሐፍ ደረጃ በብዙ መልኩ ለማስረዳት ይቻላል፡፡ ለምሳሌ ያህል ግን ሌላ መጨመር ይቻላል፡፡ የቆላም ሆነ የደጋ ወንድ አጋዘኖች በተፈጥሮ የሚያበቁሏቸው ቀንዶች  ቅዝቃዜ በመሳብ እንዲያግዛቸው ነው፡፡ በአንፃሩ ሴትዋን አጋዘን በተፈጥሮ ቀንድ የነሳት ደግሞ እንዳይቀዝዛት ነው፡፡ በሌላ በኩል ጥቁር ቀለም ሙቀት ይስባል የሚለውን መመልከት ይቻላል፡፡ የደጋ ከብት ጥቁር ሲሆን፤ የቆላ ግን ነጭ ነው፡፡ ይህን በሰው ልጅ ልንተረጉመው እንችላለን፡፡ በአለባበስ ደረጃም በሁለቱ ፆታዎች ሊኖር የሚያስፈልገውን ምቹነት በቀለማት ምርጫ ብቻ ሳይሆን በአለባበስ ፋሽን መወሰንም ይቻላል፡፡  በሙቀት ቦታ ወንድ ተነፋነፍ ወይም ሽርጥ ቢለብስ በተቃራኒው ደግሞ ሴት አጣብቂኝ ሱሬ መልበሷ ይበጃታል፡፡ የአለባበስ ሁኔታዎቹ አየሩን እንዲላመዱ እና እንዲቋቋሙ ያደርጋል፡፡  የሙቀት ወቅት አለባበስ ሳይንሳዊውን አቅጣጫ ከስነ-ተፈጥሮ የምቾት መጠበቅ ባህል ጋር አዛምዶ መስራቱን ያመለክታል፡፡
በአጠቃላይ በፆታ ልዩነት ፤ በተፈጥሮ ባህርይ፤ ከአለባበስ እና ቀለማት አንፃር በሚፈጠሩ ሁኔታዎች አትሌቲክሱን በምርምሮች እየደገፉ መስራት ያስፈልጋል ፡፡ ውጤታማ ተግባራትን ለማከናወን በስፋት የምርምር ስራዎች ለመስራት  የሰጠኋቸው አጫጭር ምሳሌዎች መነቃቃት እንዲፈጥሩ ያህል ነው፡፡
የፆታ ሁኔታ ብቻ ሳይሆን ተክለሰውነትም በአትሌቲክስ ውጤታማነት ላይ ከፍተኛ ትርጉም አለው፡፡ በምርምሮችዎ ይህን ጉዳይስ እንዴት አገናዝበውታል፡፡ በሰውነት መርዘምና ማጠር ፤ መክበድና መቅለል የውጤት ልዩነት ይፈጠራል?
የወንድና የሴት ልዩነቱ እንደተጠበቀ ሆኖ ስለቁመት ወሳኝነት በምሳሌ ረጅም አትሌት ልንወሰድ እንችላለን፡፡ በውድድር ላይ  ሙቀት ሲሆንና ሲዘቀዝቅ አትሌቱ ፋይዳና መሰናክል ይገጥመዋል፡፡ በሙቀት ከሁሉም ረዘም ብሎ ስለሚታይ በቂ ንፋስ እያገኘ ፋይዳ ይሆንለታል፡፡  የአየር ሁኔታ ብርዳማ ከሆነ ደግሞ  በቁመቱ መርዘም የበሳ ብርድማ ንፋስ አብዝቶ ስለሚያገኘው ተጎጂ ይሆናል፡፡
መክበድ መቅለልን የማየው ያው ከከናፊ ወፎች ጋርም ተዛምዶ ስላለው ነው፡፡ አውሮፕላንም እንደወፎቹ ሁሉ ቀላል ነው፡፡ በሩጫ የሚታወቁት አዳኝ እንስሳት ለምሳሌ ነብር እንደተነሳ 80 ኪ.ሜ. ፍጥነት ላይ የሚደርሰው ክብደቱ ቀላል በመሆኑ ነው፡፡ በአንድ ወቅት በክብደት ጉዳይ ላይ ከአንድ ታዋቂ አሰልጣኝ ጋር ብዙ ተከራክረናል፡፡ አሰልጣኙ አትሌቶች ውጤታማ እንዲሆኑ አስከመጨረሻው መክሰትና መቅለል አለባቸው ነበር ያሉኝ፡፡ ከምሩጽ ጋር የሮጠውን ሙሃመድ ከዲርን እንደምሳሌ በማንሳት ነበር፡፡ ቅለትም ሆነ ክብደት የራሱ የታችና የላይ ክፍል አለው፡፡ በአሃዝ ተንትኖ ለማስቀመጥ የምርምር ውጤት ያስፈልጋል፡፤ እንደ ሰው ባህሪይ የሚመገበው ምግብና የብረት ክምምችትም ይወሰናል፡፡ አንበሳ ከባድ ሆኖም ፈጣን ሯጭም ነው፡፡  አንበሳና ነብር ደም ጠጥተው ስጋ በል ናቸው፡፡ የሚወዱት ስጋና ደም ደግሞ የአዋልዲጌሳ /መቃብር ቆፋሪ/ ምስጥን ነው፡፡ ምስጥ የክብደትዋን 10 እጅ መሸከም የምትችለው የበዛ የብረት ክምችት ስላላት ነው፡፡  በሰውነት ውስጥ የሚገኝ ብረት(ፊርቲን) መርዛማ ያልሆነውና የሚሙዋማው ማለት ነው፤  በቀይ ደም ሴል ሄዶ ከሳንባ የሚወሰድ ኦክስጅን በማብዛት ትንፋሽ እንዳያጥረን ያረጋል፡፡ በመሆኑ በዚህ ዓይነት ተፈጥሮ የታደሉ ትንፋሽ ከመቁረጥ ተፋላሚያቸውን ትንፋሸ በማስቆረጥ የውጤት ፋይዳቸውን ይጨምራሉ፡፡
….. ይቀጥላል

    - ተቃዋሚዎች ህጉ እንዳይሻሻል ዘመቻ እናደርጋለን ብለዋል
   የሩዋንዳው ፕሬዚዳንት ፖል ካጋሜ ህጉ ከሚፈቅድላቸው ውጭ ለ3ኛ ዙር የስልጣን ዘመን በምርጫ ለመወዳደር መወሰናቸው  ውዝግብ መፍጠሩን ተከትሎ፣ የአገሪቱ ፓርላማ ህገ መንግስቱ ተሻሽሎ ካጋሜ በምርጫ ይወዳደሩ በሚል ያቀረበውን ሃሳብ፣ የሩዋንዳ ጠቅላይ ፍርድ ቤት እንዳጸደቀው ኒውዮርክ ታይምስ ዘገበ፡፡
ፍርድ ቤቱ ዲሞክራቲክ ግሪን ፓርቲ የተባለው የአገሪቱ ተቃዋሚ ፓርቲ፣ ፕሬዚዳንት ካጋሜን በስልጣን ላይ ለማቆየት ሲባል በህገ መንግስቱ ላይ ምንም አይነት ለውጥ እንዳይደረግ ያቀረበውን አቤቱታ ውድቅ በማድረግ፣ በህገ መንግስቱ ላይ ማሻሻያ እንዲደረግ መወሰኑን ዘገባው ገልጧል፡፡
የአገሪቱ ፓርላማ አባላት ባለፈው ሃምሌ ህገ መንግስቱ እንዲሻሻልና ጉዳዩ በህዝበ ውሳኔ እልባት እንዲያገኝ መስማማታቸውን  የዘገበው አይቢ ታይምስ በበኩሉ፣ ድምጻቸውን ከሰጡ ሩዋንዳውያን መካከል 70 በመቶ የሚሆኑት ወይም 3.7 ሚሊዮን ያህሉ የአገሪቱን ፕሬዚዳንት የስልጣን ዘመን የሚገድበው የህገ መንግስቱ አንቀጽ እንዲሻሻል ድጋፍ መስጠታቸውን ገልጧል፡፡
አንዳንድ አስተያየት ሰጪዎች ግን በርካታ ሩዋንዳውያን ህገመንግስቱ ይሻሻል የሚል ድምጽ የሰጡት በመንግስት ሃይሎች ተገደው ነው ሲሉ ውሳኔውን የነቀፉ ሲሆን፣ የተቃዋሚው ዲሞክራቲክ ግሪን ፓርቲ ፕሬዚዳንት ፍራንክ ሃቢኔዛ በበኩላቸው፤ ፍርድ ቤቱን ይግባኝ እንደሚጠይቁ ጠቁመው፣ በህገ መንግስቱ ላይ ምንም አይነት ለውጥ እንዳይደረግና ካጋሜ ዳግም በምርጫ እንዳይወዳደሩ ለመገደብ ዘመቻ እንደሚጀምሩ ተናግረዋል፡፡

 የፌስቡኩ መስራች ማርክ ዙክበርግ በተለያዩ የአለማችን አገራት ለሚገኙ የስደተኞች መጠለያ ጣቢያዎች፣የኢንተርኔት አቅርቦት ለማሟላት እየተንቀሳቀሰ መሆኑን እንዳስታወቀ አሶሼትድ ፕሬስ ዘገበ፡፡ዙክበርግ ባለፈው ቅዳሜ በተከናወነው የተባበሩት መንግስታት ድርጅት ጠቅላላ ጉባኤ ላይ ተገኝቶ ባደረገው ንግግር፣ በስደተኞች መጠለያ ጣቢያዎች ውስጥ የሚገኙ ዜጎችን ከተቀረው አለም ጋር በመረጃ ለማስተሳሰር፣ የኢንተርኔት አቅርቦት የማሟላት እቅድ እንዳለው አስታውቋል፡፡
የኢንተርኔት አቅርቦት መሟላቱ ስደተኞች ከእርዳታ ድርጅቶችና ከለጋሾች የተሻለ ድጋፍ እንዲያገኙ የራሱን እገዛ ያደርጋል ያለው ዙክበርግ፣ በርቀት ከሚገኙ ቤተሰቦቻቸው ጋር እንዲገናኙም ያስችላቸዋል ብሏል፡፡
 ዙክበርግ በአለማ አቀፍ ደረጃ የኢንተርኔት ትስስር ለመፍጠርና ከ5 ቢሊዮን በላይ የተለያዩ አገራት ዜጎችን ተጠቃሚ ለማድረግ የሚያስችል ኢንተርኔት ዶት ኦርግ የተሰኘ ፕሮጀክት ከሌሎች አጋር ድርጅቶች ጋር በመተባበር እ.ኤ.አ ከ2013 ጀምሮ መተግበር እንደጀመረም ዘገባው አስታውሷል፡፡