Administrator

Administrator

Saturday, 27 January 2024 00:00

”የደጋ ሰው” በተሰኘው

አልበም ላይ ዛሬ ውይይት ይካሔዳል

”የደጋ ሰው” በተሰኘው አዲስ የሙዚቃ አልበም ላይ ውይይት እንደሚካሔድ፣ የኢትዮጵያ ሳይንስ አካዳሚ አስታወቀ፡፡
ዛሬ ከቀኑ 8  ጀምሮ ጉለሌ በሚገኘው የአካዳሚው የብላቴን ጌታ ኅሩይ ወልደ ሥላሴ የሥነጥበባት ማዕከል የሚደረገውን ውይይት፣ ደራሲና ሃያሲ ይታገሱ ጌትነት የሚመሩት ሲሆን፤ የሙዚቃ ባለሙያው ሰርፀ ፍሬስብሐት፣ መምህርና የሙዚቃ ደራሲው ኢዩኤል መንግሥቱ ለውይይት መነሻ የሚሆን ጽሁፍ ወይም ሃሳብ ያቀርባሉ ተብሏል፡፡ በውይይት መድረኩ ላይ ድምጻዊቷ የማርያም ቸርነትት እንደምትሳተፍ ታውቋል፡፡  

የአርቲስት ካሣሁን እሸቱ “ይሁን” የተሰኘ የሙዚቃ አልበም ትላንት መለቀቁ ተገለጸ፡፡ አርቲስቱ የአልበሙን መለቀቅ አስመልክቶ ባለፈው ሰኞ  በሸራተን አዲስ ጋዜጣዊ መግለጫ የሰጠ ሲሆን፤ ኪነት ኢንተርቴይንመንት ከአዲስ ሚውዚክ መልቲሚዲያ ጋር በመተባበር ይህን ”ይሁን” የተሰኘ  የድምጻዊ ካሣሁን እሸቱ የሙዚቃ አልበም ለማስመረቅ በዝግጅት ላይ መሆናቸው ተጠቁሟል፡፡በዚህ የድምጻዊው አዲስ የሙዚቃ አልበም ላይ በግጥም እራሱ አርቲስት ካሣሁን እሸቱ፣ አንጋፋው ድምጻዊ ቴዎድሮስ ካሣሁን (ቴዲ አፍሮ) እና መሰለ ጌታሁን፤ በዜማ ደግሞ አቤል ጳውሎስ፣ ድምጻዊ ካሣሁን እሸቱ፣ ቴዎድሮስ ካሣሁን (ቴዲ አፍሮ) የተሳተፉ ሲሆን፤ በቅንብር አበጋዝ ክብረወርቅ ሺዎታ፣ አቤል ጳውሎስ፣ ካሙዙ ካሣ፣ ሚካኤል ሃይሉና መሃመድ ኑርሁሴን፤ በሚክሲንግ ሰለሞን ሃ/ማርያምና ፍሬዘር ታዬ፤ በማስተሪንግ ደግሞ አበጋዝ ክብረወርቅ ሺዎታ ተሳትፈውበታል፡፡አዲሱ አልበም 15 በተለያዩ ስልቶች የተቀነቀኑ ዘፈኖችን ያካተተ ሲሆን፤ ድምጻዊው በዚህ አልበም ስለ ሃገር፣ ስለ ምስጋና  እና ስለ ተስፋ ማቀንቀኑ ተነግሯል፡፡
እዚህ ለመድረሴ የጋሞ አባቶች ምርቃት የመንገዴ ጠራጊ ነው ብሎ የሚያምነው ድምጻዊ ካሣሁን እሸቱ፤ ተወልዶ ያደገው በውቧ የመዋደድና የመከባበር ተምሳሌት በሆነችው አርባምንጭ ከተማ ነው፡፡
 አዲስ አበባ ከመጣ በኋላ የሙዚቃ ህይወቱን የጀመረው ቦሌ አካባቢ በሚገኘው ላየን ክለብ ከላፎንቴኖች ጋር በተዘጋጀው ፕሮግራም ላይ ነበር፡፡ ድምጻዊው በአንቲካ ባርና ሬስቶራንት ለ6 ዓመት፣ በመሣፍንት ቤት ደግሞ ለ5 ዓመታት በድምጻዊነት መሥራቱን ለማወቅ ተችሏል፡፡
የድምጻዊ ካሣሁን እሸቱ ”ይሁን“ የተሰኘ አዲስ የሙዚቃ አልበም፣ በትላንትናው ዕለት በራሱ የዩቲዩብ ቻናል (ካሣሁን እሸቱ ካስዬ) እንደሚለቀቅ ተጠቁሟል፡፡  

Sunday, 28 January 2024 20:22

ዘመናዊ ብልጦች

ዘመናዊ ብልጦች
ታጋይ እንጂ ትግል አይሞትም እያሉ
ታግለው ሲያታግሉ
ፎክረው የማሉ ታጋይ ሲፈነቸር
ትግሉም ፍግም ሲል
ይኸው ይኖራሉ።
(ሙሉነህ መንግሥቱ)

Sunday, 28 January 2024 20:20

አይን አዋጅ

ወላድ በድባብ ትሂድ
እንጂ ቆንጆ ሞልቶ ባሻገር፣
እኔ ዓይን አዋጅ ሆኖብኝ
እስቲ በምርጫ ልቸገር?
(መዓዛ ብሩ

አንድ ጊዜ አንድ የትግያ (Wrestling) ጥበብ አዋቂ፤ ለአንድ ተማሪው፤ “ና ትግያ ላስተምርህ” ይለዋል፡፡
ተማሪውም፤
“ምን ያህል የአስተጋገል ዘዴ ታውቃለህ?” ሲል ይጠይቀዋል፡፡
አስተማሪውም፤
“360 የትግያ አይነቶች እችላለሁ” አለው፡፡
“እነዚህን ሁሉ ለመማር ምን ያህል ጊዜ ይፈጅብኛል?”
“እሱ እንደቅልጥፍናህ ነው፡፡ አንዱ ጥበብ ከሌላኛው ጋር የሚያያዝ ነው፡፡ እስቲ ሞክረውና ከዚያ ጊዜውን ለመገመት ትችላለህ” ሲል ይመልስለታል፡፡
ከዚህ በሁዋላ መምህሩ ወጣቱን ማስተማር ጀመረ፡፡ የተወሰነ ዓመታት ፈጅቶበት ወጣቱ 359 የትግያ ጥበብና ዘዴዎችን ተማረ፡፡ የመጨረሻዋን ጥበብ ግን ሳይማር ቀረ፡፡ ወራትና ዓመታት እየገፉ በሄዱ ቁጥር ወጣቱ በትግያ እየተራቀቀ በገመድ ቀለበት ውስጥ የመጡ ተጋጣሚዎችን ሁሉ ተራ በተራ እየተጋጠመ እያሸነፈ የተዋጣለት አሸናፊ ሆነ፡፡ ዝናንም አተረፈ፡፡ በዚህም ከፍተኛ ኩራት ተሰማው፡፡
አንድ ቀን ሰው ሁሉ በተሰበሰበበት ለአስተማሪው፡-
“ሰማህ ወይ መምህር፤ እስከዛሬ ባስተማርከኝ ጥበብ በጣም ተራቅቄበታለሁ፡፡ ወደ ትግያ የገመድ ቀለበቴ የገቡትን ተጋጣሚዎች ሁሉ አንድ ባንድ እያነሳሁ አፍርጬ በአሸናፊነት ተወጥቻለሁ፡፡ አንተንም ቢሆን በማክበር ነው እንጂ ብገጥምህ እጥልሀለሁ” አለው፡፡
መምህሩም በዚህ በተማሪው ድፍረት በጣም ተናደደና፡-
“ለመሆኑ አሁኑኑ የትግሉ ገመዱ እንዲዘጋጅ ባደርግ ለመታገል ዝግጁ ነህ?” ሲል ጠየቀው፡፡
ተማሪውም፡-
“ከተዘጋጀሁ ቆይቻለሁ” አለው፡፡
መምህሩ በተማሪው መልስ በጣም ተበሳጭቷል፡፡
“እንግዲያው በል ና የአገሩ ሡልጣን ፊት ሰው ባለበት አደባባይ ላይ እንጋጠማለን” አለውና ወደ መታገያው የገመድ ቀለበት ውስጥ ገቡ፡፡
እንደተጀመረ ወጣቱ እየጮኸና እየዘለለ የመምህሩን ወገብ ጥብቅ አድርጎ ይዞ ሊጥለው ይወዘውዘው ጀመረ፡፡ ሆኖም አልጣለውም፡፡
እንደገና በሌላ ወገን ይይዘውና ዘርጥጦ ሊጥለው ይሞክራል፡፡ አሁንም አልሆነለትም፡፡
ወጣቱ 359ኙንም የመታገያ ዘዴዎቹን ተጠቅሞ ሊጥለው ሞክሮ ሳይሳካለት ቀረ፡፡ በኋላ መምህሩ መጠናከር ጀመረ፡፡ በመጨረሻም፡-
ወጣቱን በሁለት እጆቹ ወደ ላይ አንስቶ ቁልቁል ወደ መሬት ወረወረው፡፡ ወጣቱ ተሰባበረ፤ ሰውነቱ ደቀቀ፡፡
ተመልካቹ አካባቢውን በሆታ ሞላው፡፡
ሡልጣኑ መምህሩን አሰጠርቶ፡-
“ይሄ ወጣት በከተማችን የተነገረለትና በጣም እየጠነከረ የመጣ ነው፡፡ ማንም ሲጥለው አላየሁም፡፡ አንተ አርጅተሃል፡፡ አቅምህ ደክሟል፡፡ ታዲያ እንዴት ልትጥለው ቻልክ?” ሲሉ ጠየቁት፡፡
መምህሩም፤
“ሡልጣን ሆይ! ወጣቱን ሳስተምረው 359 ጥበቦችን ነው ያስተማርኩት፡፡ ይቺ አሁን የተጠቀምኩባት ጥበብ 360ኛዋ ናት፡፡ ይቺ የኔ የራሴ የክቴ ናት፡፡ ለእንዲህ ያለው ጊዜ ነው የምጠቀምባት፡፡ አንድ ጊዜ አንድ የቀስት ውርወራ አስተማሪ ያለ የሌለውን ጥበብ በሙሉ አስተምሮ ሲያበቃ አንዱ ተማሪው ውድድር ገጥሞ አሸነፈው፡፡ አስተማሪውም ‘ሳይቸግረኝ ያለኝን ዘዴ ሁሉ ሰጥቼ ነው ጉድ የሆንኩት!’ አለ ይባላል” ሲል በምሳሌ አስረዳቸው፡፡
***
ዘዴና ጥበብን ሁሉ ሙልጭ አድርገው ሰጥተው ባዶ መቅረት ኋላ ማጣፊያ ሊያሳጥር እንደሚችል ነው ከላይ ያለው አፈ-ተረት የሚነግረን፡፡ “ሁሉን ቢናገሩት ሆድ ባዶ ይቀራል” እንዲል የአበሻ ተረት፡፡ አሊያም በዚህ በውድድር ዓለም ተወዳዳሪህ ወይም ተፎካካሪህ ውሎ አድሮ ምን እንደሚያስብ በማጤን የክትህ የሆነ በልጦ መገኛ ዘዴ ሊኖርህ እንደሚገባ አስተውል ማለቱ መሆኑን እረዳለን፡፡ አንድም ብዙ ባሸነፍክ ቁጥር አቅምህን ሳትለካ መንጠራራት አሊያ ደግሞ አላስፈላጊ ግጥሚያ ውስጥ ገብቶ መቀናጣት ለምን አይነት ሽንፈት እንደሚዳርግ እንድናስተውል ይጠቅመናል፡፡ በሀገራችን በርካታ ፍልሚያዎች ወይ የእንቅስቃሴ ሂደቶች ውስጥ የባላንጣን ስስ ብልት በማየት በጎላ ፕሮፓጋንዳ ላይ ብቻ በማተኮር ሲደነቋቁሩ መክረም፣ ሀሰተኛ ቅስቀሳን በመደጋገም ከጊዜ ብዛት ይታመንልኛል ብሎ ማሰብ፣ ያገኙትን ትንሽ ድል እጅግ አጋኖ ግነን በሉኝ ማለት አልያም በጊዜያዊ ድል መኩራራት ወዘተ  ከግብ ላለመድረስ ጥቂት ተጠቃሽ ምክንያቶች ናቸው፡፡ ዳሩ ግን ከታሪክ ለሚማር ታሪካዊ እሴቶች ናቸው፡፡ ከቶውንም በሌሎች ላይ የምንሰነዝረው ትችትና ጥቆማ እኛ  ከምንሰራው ተጨባጭ ተመክሮ አንፃር ተግባራዊ ትርጉሙ ምንድን ነው የሚለው ጥያቄ ግንዛቤ ውስጥ ቢገባ ደግ ነው፡፡ በወንድምህ ዐይን ውስጥ ያየኸውን ጉድፍ…. እንዲል መፅሀፍ፡፡
ከማናቸውም ማህበራዊና ፖለቲካዊ ሂደት የምናገኘው ተመክሮ ጠርዝ ያለው መሰረት ይሆን ዘንድ ከ359ኛው ጥበብ ባሻገር 360ኛውን ማሰብ ተገቢ ነው፡፡ የሀገራችን ችግሮች ሁልቆ-መሳፍርት ናቸው፡፡ ሁልቆ-መሳፍርት ጥበብንና በብዙ ጭንቅላት ማሰብ ይጠይቃሉን፡፡ እኔ ብቻ ነኝ መፍትሄ ልሰጣቸው የምችለው ማለት ብዙ አያራምድም፡፡
ሆደ-ሰፊና ተቻቻይ ከሁሉ ጋር ተባብሮ፣ ተግባብቶ ሙያን አክብሮ ልምድን በአግባቡ ተጠቅሞ መንቀሳቀሰስ አግባብ ነው፡፡ ያቅም፣ ካቅም በላይም አሊያም ካቅም በታች፣ አቅሜ ነው ብሎ መዋሸት ቀኑ ሲደርስ “ምላጭ የዋጠ ማስወጣቱ ይጨንቀዋል” የሚባለውን ተረት ነው የሚያረጋግጠው፡፡
አያሌ በሀገርም ደረጃ፣ በዓለምም ደረጃ የምንገባቸው ውሎች የምናልማቸው ትርፎች፣ የምናቅዳቸው ዲፕሎማሲያዊ አካሄዶች፣ “እዚያ ቤት እሳት አለ” ብለን የምናጤናቸው ሊሆኑ ይገባል፡፡ ዐይነ-ውሃቸው የሚያምር ወይም ከጊዜያዊ ጣር የሚያላቅቁን የሚመስሉ አያሌ ጉዳዮች ኋላ የማይያዙ የማይጨበጡ እዳዎች፣ ውል-የሌላቸው ችግሮች እንዳይሆኑ መጠንቀቅ ይገባል፡፡ አብዛኞቹ የኢኮኖሚ መስተጋብሮች ረጋ ተብለው ሲታሰቡ፣ ሙስናዊ ቀዳዳዎቻቸው የበዙ መሆናቸው ብቻ ሳይሆን፣ እያንዳንዳቸው ቀዳዳዎች እያደር እየሰፋ የሚሄዱ እንዳይሆኑ ግለሰቦች ላይ ከጣለው ፖለቲካዊ እምነት ባሻገር በሀገር መንፈስ ማውጠንጠን፡፡ ሲሞን ቦሊቫር የተባለ የአዲሲቱ የላቲን አሜሪካ ሪፑብሊክ መሪ “በሦስቱ ጥምር ችግሮች ማለትም - ድንቁርና ጭቆናና ሙስና ተጠፍረን ታስረን፣ ትምህርት፣ ሥልጣንና  ሥነምግባር ሊኖረን አልቻለም፡፡ እናም የተማርነው ባልሆኑ መምህራን ስለሆነም ያገኘናቸው ልምዶችም ሆኑ ያናናቸው ምሳሌዎች ወደ ጥፋት የማምራት ባህሪ ነው ያላቸው፡፡ ከጉልበት የበለጠ በመታለል ተጠቅተናል፡፡ ሙስናም ከአጉል አምልኮ የበለጠ ቁልቁል አርጎናል፡፡…. ምኞትና ተንኮል ሁነኛ የፖለቲካ፣ የኢኮኖሚ ወይም የሲቪክ እውቀት የሌላቸው ሰዎች፣ ልምድ የለሽና በቶሎ አማኝ ያደርጋቸዋል፡፡ ቅዠቶቹን እውን አድርገው እንዲያዩ ያደርጋቸዋል፡፡ ፈቃድን ከነፃነት ያምታታባቸዋል፡፡ ክህደትን ከጀግንነት ያወነባብድባቸዋል፡፡ በቀልንም ከፍትህ ያምታታባቸዋል” ይላል፡፡ ከዚህ ይሰውረን ማለት ደግ ነው፡፡
ነባራዊና እሙናዊውን ቀና መንገድ ይዞ መጓዝ ከበሽታ ያድነናል፡፡ ከኢኮኖሚ ድቀት ያወጣናል፡፡ ከስህተታችን እንድንማር ያደርገናል፡፡ ከሁሉም በላይ ግን የገባነውን ቃል እንድናከብር ያግዘናል፡፡ ዞሮ ዞሮ ግን የምንለው ከምናደርገው ካልተገናኘና አልፎ ተርፎም አገርና ህዝብን የሚጎዳ ከሆነ “ምላስ ደህና ቦታ ተቀምጣ፣ ጭንቅላት ታሰብራለች” የሚለውን አባባል ነው የሚተረጉም፡፡

“የኦሮሚያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን መንበረ ጴጥሮስን መሥርተናል፤” በሚል፣ በሸገር ከተማ አስተዳደር፣ ባለፈው ማክሰኞ መግለጫ ሲሰጡ በፖሊስ ቁጥጥር ሥር የዋሉ ግለሰቦች፣ ፍርድ ቤት ቀርበው የዐሥር ቀን ተጨማሪ የምርመራ ቀጠሮ ተሰጥቶባቸዋል።ፖሊስ፣ ከትላንት በስቲያ ኀሙስ፣ በሸገር ከተማ አስተዳደር የናኖ መልካ የመጀመሪያ ፍርድ ደረጃ ቤት ባቀረባቸው ግለሰቦች ላይ፣ 14 ቀናትን ለምርመራ ጠይቆባቸው፣ ፍርድ ቤቱ 10 ቀን መፍቀዱን ምንጮች ገልጸዋል፡፡

ባለፈው ዓመት ጥር 14 ቀን 2015 ዓ.ም. “የኦሮሚያ እና ብሔር ብሔረሰቦች ሲኖዶስ” መሥርተናል ብለው በተደረገው ስምምነት ከተመለሱት 25 መነኮሳት ውስጥ አራቱ አባቶች፣ በአሁኑ እንቅስቃሴ ውስጥ እንደሚገኙበት ታውቋል።“መንበረ ጴጥሮስን መሥርተናል” በማለት መግለጫ ከሰጡት ውስጥ ሦስቱ፣ በዚያው ዕለት ምሽት በመንግሥት የጸጥታ ኀይሎች ተይዘው የታሰሩ ሲሆን፣ የሸገር ከተማ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ብፁዕ አቡነ ሳዊሮስ፣ የመንበረ ፓትሪያርክ ጠቅላይ ቤተ ክህነት፣ ኢ-ቀኖናዊ ድርጊት በፈጸሙት በእነዚኽ ግለሰቦች ላይ ክስ እንዲመሠረት ጠቅላይ ሥራ አስኪያጅ ብፁዕ አቡነ አብርሃምን በቃል እንደጠየቁ፣ የቅርብ ምንጮች ለአዲስ አድማስ ገልጸዋል፡፡


ባለፈው ዓመት፣ በጠቅላይ ሚኒስትሩ አወያይነት፣ በሕገ ወጥ መንገድ ኤጲስ ቆጶስነት የተሾሙት መነኮሳት፣ ከመሰል ድርጊቶች ለመታቀብ ከቅዱስ ሲኖዶሱ ጋራ በተደረሰው ስምምነት፣ ውግዘቱ ተነሥቶላቸው ሥልጣነ ክህነታቸው እንደተመለሰላቸውና የሥራ ላይ መብታቸው እንደተጠበቀላቸው መገለጹ ይታወሳል።
ዓመቱን ጠብቀው፣ ከቤተ ክርስቲያኒቱ ቀኖና ውጪ እና ስምምነቱን በሚፃረር መልኩ እንደሰጡት በተነገረው መግለጫ ለእስር መደረጋቸው ለብዙዎች አነጋጋሪ ኾኗል።
ከእንቅስቃሴው ጋራ በተያያዘ፣ እስከ አሁን በቁጥጥር ሥር የዋሉት መነኮሳት እና ሌሎች የ”መንበረ ጴጥሮስ ምሥረታ” አስተባባሪዎች ናቸው የተባሉ ግለሰቦች ቁጥር ዘጠኝ እንደደረሰ ተመልክቷል።

ብልፅግና ፓርቲ የኢንፎርሜሽን መረብ ደህንነት አገልግሎት ዋና ዳይሬክተር የሆኑትን አቶ ተመስገን ጥሩነህን የፓርቲው ም/ፕሬዚዳንት አድርጎ የሾመ ሲሆን፤ ፓርቲውን በም/ፕሬዚዳንትነት ሲያገለግሉ የቆዩትን ም/ጠቅላይ ሚኒስትርና የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር አቶ ደመቀ መኮንን በክብር አሰናብቷል።አቶ ተመስገን ጥሩነህ ከዚህ ቀደም የአማራ ክልል ፕሬዚዳንት ሆነው ለጥቂት ጊዜ ካገለገሉ በኋላ የኢንፎርሜሽን መረብ ደህንነት አገልግሎት ዋና ዳይሬክተርና የብልፅግና ፓርቲ ማዕከላዊ ኮሚቴ አባል ሆነው እያገለገሉ ይገኛሉ።ብልፅግና ትላንት ጥር 17 ቀን 2016 ዓ.ም ቀትር ላይ ይፋ እንዳደረገው፤ ፓርቲው የአሰራር ስርዓትንና የአመራር መተካካትን መርህ በመከተል የፓርቲው ም/ፕሬዚዳንት ሆነው ሲያገለግሉ የነበሩትን አቶ ደመቀ መኮንን በክብር አሰናብቶ አቶ ተመስገን ጥሩነህን በአብላጫ ድምፅ መርጧል።

በአማራና ኦሮሚያ ክልሎች የሚፈጸሙ የድሮን ጥቃቶች ንፁሃን በሚኖሩባቸው አካባቢዎች ላይ ጉዳት እያደረሱ ነው ያለው የኢትዮጵያ ዜጎች ለማኅበራዊ ፍትህ (ኢዜማ) በመንግስት የፀጥታ ሃይሎችና ታጣቂዎች መካከል በሚደረጉ ጦርነቶች ዜጎች ህይወታቸውን ማጣትን ጨምሮ ክፉኛ እንደተጎዱ አመልክቷል።
ኢዜማ ይህንን ያለው ወቅታዊ ጉዳዮችን አስመልክቶ ከትላንት በስቲያ ሐሙስ በሰጠው ጋዜጣዊ መግለጫ ነው።የዜጎች ደኅንነት፣ የሰብዓዊ እና ዴሞክራሲያዊ መብቶች ይዞታ፣ በትግራይ ክልል የተከሰተው ድርቅና ረሀብን እንዲሁም በአማራ እና በኦሮሚያ ክልሎች የቀጠለውን ጦርነት በተመለከቱ ጉዳዮች ላይም አቋሙን አስታውቋል።በአማራና በኦሮሚያ ክልሎች እየተደረገ ያለው ጦርነት “ከፍተኛ ዋጋ እያስከፈለ” መሆኑን በመግለጫው የጠቀሰው ፓርቲው፤ “በጦርነቱ እየተሳተፉ የሚገኙ አካላት ሳይቀር” ይህንን ጉዳት ይገነዘቡታል ብሎ እንደሚያምን ገልጿል።
በክልሎቹ ባለው ጦርነት ምክንያት የግብርና፣ የትምህርት፣ የንግድ፣ የኢንቨስትመንትና የቱሪዝም እንቅስቃሴዎች እንደተስገጓጎሉ ጠቅሶ፤ በክልሉ ውስጥ የሚገኙ ዜጎችም ለችግር መጋለጣቸውን ጠቁሟል።ከዚህም ባሻገር በክልሎቹ ውስጥ ከሚካሄደው ጦርነት ጋር በተያያዘ በሚወሰዱ ወታደራዊ ኦፕሬሽኖች “ንጹሃን ዜጎች ሰለባ” እየሆኑ እንደሆነ ኢዜማ በመግለጫው አስታውቋል።ኢዜማ ከዐይን እማኞች በሰበሰበው መረጃ መሠረት፤ በተለይም በድሮን የሚደረጉ የአየር ላይ ጥቃቶች ንፁሃን በሚኖሩባቸው አካባቢዎች ላይ ጉዳት እየደረሱ መሆኑን ማረጋገጡን ገልጿል።“ከመንግሥት ጋር የሚፋለሙ ታጣቂዎችም ‘ከተሞችን እንቆጣጠራለን’ በሚል በሚያደርጉት የከተማ ውስጥ ውጊያ በሰው ሕይወትና ሀብት ላይ ከፍተኛ ጉዳት እየደረሰ ነው” ሲል ኢዜማ ታጣቂዎችን ከሷል።
“አሁን ያለው ሁኔታ በዚሁ ከቀጠለ ከዚህም የባሱ ለአገር ህልውና አስጊ የሆኑ ቀውሶች መፈጠራቸው የሚቀር አይመስልም። በእነዚህ ጦርነቶች እንደ አገር ሁላችንም ከስረናል። ያተረፈም ካለ ኢትዮጵያን በዐይነ ቁራኛ የሚከታተሉ ጠላቶቿ ብቻ ናቸው” ሲል ስጋቱን ገልጿል።
ኢዜማ ለዜጎች ሰላምና ደኅንነት ማጣት መንግሥትና ታጣቂ ኃይሎችን ተጠያቂ አድርጓል። ባለፉት ኅዳርና ታኅሣሥ ወራት በኦሮሚያና ጋምቤላ ክልል በታጣቂዎች የተፈጸሙ ሰባት ጥቃቶችን የጠቀሰው ፓርቲው፤ በእነዚህ ጥቃቶች መንግሥት የዜጎችን ደኅንነት ማስጠበቅ አለመቻሉን አስታውሷል።ኢዜማ በሰሞኑ መግለጫው፤ የመንግሥት የፀጥታ ኃይሎችና በትጥቅ ትግል ላይ ያሉ ታጣቂዎች “ንጹሃንን የሚጎዳ ወታደራዊ ጥቃት መፈጸም” እንዲያቆሙ አሳስቧል።
“መከላከያ ሠራዊትን እየወጋችሁ ያላችሁ ታጣቂዎችም የጠመንጃው መንገድ ደጋግሞ አክስሮናልና ጠመንጃችሁን አስቀምጣችሁ ቢያንስ “ቆመንለታል” የምትሉትን ሕዝብ ከገባበት አጠቃላይ ቀውስ ለማውጣት የየበኩላችሁን ድርሻ እንድትወጡ ጥሪ እናቀርባለን” ብሏል-ኢዜማ በመግለጫው።
መንግሥትም “በፀጥታ መዋቅሩ ውስጥ ያለውን ዘርፈ ብዙ እንቅስቃሴ በሚገባ” እንዲመረምር ፓርቲው አሳስቧል። “ጦርነት እንዲቆም ትጥቅ ላነሱ አካላት ሀቀኛ የሆነ ይፋዊ የሰላም ጥሪ” መንግስት እንዲያቀርብም በመግለጫው ጠይቋል።

በሀገራችን እየታየ ያለውን የትምህርት ጥራት መጓደልና የተማሪዎች ውጤት ማሽቆልቆል ተከትሎ የትምህርት ጥራትን ለማስጠበቅ ታስቦ የተመሰረተው “ዩቶፒያስ ስቱደንትስ” አጋዥ የትምህርት መተግበሪያ አገልግሎት ላይ መዋሉን የድርጅቱ ባለቤቶች ገለፁ። የድርጅቱ ባለቤቶች ይህን የገለፁት ትላንት ረፋድ ላይ በዓለም ሲኒማ ለመገናኛ ብዙሃን ባለሙያዎች በሰጡት ጋዜጣዊ መግለጫ ነው።በ2015 ዓ.ም የተመሰረተው “ዩቶፒያስ ስቱደንትስ”፤ የመማር ማስተማር ሂደቱን ቀላል፣ ምቹና ቀልጣፋ የሚያደርጉ አሰራሮችን እየተገበረ የሚገኝ ሲሆን፣ በይፋ የተዋወቀው መተግበሪያም ከ9ኛ ክፍል ተማሪዎች የሚያገለግል እንደሆነ ተገልጿል።
መተግበሪው የስድስት ዓመት (ከ2017-2022 ያሉ) የ12ኛ ክፍል የመግቢያ ጥያቄዎችን ከእነመልሶቻቸው፣ ለጥናት የሚያገለግሉ ከ9-12ኛ ክፍል ያሉ አጋዥ መፅሐፍትን፣ 24 ሰዓት ማናቸውንም ጥያቄዎችን የሚመልስ ሰው ሰራሽ አስተውሎት (AI)፣ እንዲሁም በየጊዜው የሚዘጋጁ ሽልማት የሚያስገኙ ውድድሮችን በውስጡ ያካተተ ሲሆን፣ መተግበሪያውን ከጉግል ፕሌይ ስቶር በማውረድና  ለአገልግሎቱ በዓመት አንድ ብር በመክፈል መጠቀም እንደሚቻል ተገልጿል።
መተግበሪያው በአዲስ አበባ ትምህርት ቢሮና በኢንፎሜሽን ኮሙኒኬሽን ቴክኖሎጂ ባለሙያዎች ተገምግሞ ያለፈና ለተማሪዎች አጋዥ እንደሚሆን ታምኖበት አገልግሎት ላይ የዋለ መሆኑም ታውቋል።

ካፒታሉን ወደ 1 ቢሊዮን ብር አሳድጓል

ብሬክስሩ ትሬዲንግ አክሲዮን ማህበር ባለፉት አራት ዓመታት ከ41 ሺህ በላይ ለሆኑ ዜጎች የሰብዕና ለውጥ ሥልጠና መስጠቱንና በስልጠናው በርካታ በኢኮኖሚ ራሳቸውን የለወጡ ዜጎች ማብቃቱን አስታወቀ፡፡ ድርጅቱ ይህንን የገለፀው ባለፈው ረቡዕ ጥር 15 ከሰዓት በኋላ በሸራተን አዲስ ሆቴል ላሊበላ አዳራሽ የተመሰረተበትን 4ኛ ዓመት በዓል  ባከበረበት ወቅት ነው፡፡ብሬክ ስሩ ትሬዲንግ በ2012 ዓ.ም “ቅን” (Genuine) በተሰኘ 17 ባለ ራእይ ሰዎች ጥምረት የተቋቋመ ሲሆን፣ አላማውም ባለ ራዕይ፣ ቅን፣ ጤናማና ባለፀጋ ትውልድን መፍጠር እንደሆነ የድርጅቱ ዋና ስራ አስፈፃሚ አቶ አብዱል ፈታህ ሁሴን ተናግረዋል፡፡ ድርጅቱ በአራት ዓመት ጉዞው ዜጎች በአዎንታዊ መልኩ ሰብዕናቸውን በመገንባት በኢኮኖሚ ያደጉና ሀገራቸውን የሚጠቅሙ እንዲሆኑ እየተጋ እንደሚገኙ ዋና ሥራ አስፈፃሚው ጨምረው ገልፀዋል፡፡ ብሬክስሩ በ2.4 ሚ ብር ካፒታል ተነስቶ በአራት ዓመታት ውስጥ ካፒታልን ወደ 1 ቢሊዮን ማሳደጉንና አሁንም አክሲዮን በመሸጥ ላይ መሆኑን የገለፁት ዋና ስራ አስፈፃሚው፣ ከሰብዕና ግንባታ በተጨማሪም ወደ ተለያዩ ቢዝነሶች እየተሰማራ መሆኑንና በቅርቡ አንድ ት/ቤት መክፈቱን እንዲሁም “የኔ” የተሰኘ የሰብዕና ግንባታ ስልጠና ፕሮጀክት ማቅረቡንና በትራንስፖርት አገልግሎት ዘርፍ እንደሚሰማራም ተናግረዋል፡፡
በብሬክስሩ ትሬዲንግ አክሲዮን ማህበር አራተኛ ዓመት የምስረታ ክብረ በዓል ላይ ከፍተኛ የመንግስት የስራ ሀላፊዎች፣ የንግዱ ማህበረሰብ አባላት፣ የድርጅቱ ከፍተኛ ሀላፊዎችና አባላትን እንዲሁም ጥሪ የተደረገላቸው እንግዶች ታድመዋል፡፡

Page 10 of 695