
Administrator
በኢትዮጵያ የመጀመርያው የዲጂታል ፊርማ መተግበሪያ ይፋ ሊደረግ ነው
• አዲሱ መተግበሪያ ሰነዶች በዲጂታል መንገድ የሚፈረሙበትን መንገድ ያዘምናል ተብላል›
ቪዲቸር የቴክኖሎጂ ድርጅት፣ አዲስ ያበለጸገውን “ውለታ“ የተሰኘ የዲጂታል ፊርማ መተግበሪያ ይፋ ሊያደርግ መሆኑን አስታወቀ። “ውለታ“ በብዕር የሚደረጉ ፊርማዎችን በኤሌክትሮኒክስ ፊርማዎች በመተካት፣ ልዩ ልዩ ሰነዶች የሚፈረሙበትን መንገድ ለመቀየር ዝግጅቱን ማጠናቀቁ ተጠቁሟል።
“ውለታ“ የኤሌክትሮኒክስ መፈረሚያ፣ ለአንድሮይድ እና አይኦኤስ ተጠቃሚዎች በአመቺ ሁኔታ የቀረበ መተግበርያ መሆኑን የጠቆመው ድርጅቱ፤ከዚህ በተጨማሪም ተጠቃሚዎች በቀላሉ ሰነዶችን አዘጋጅተው መላክ የሚችሉበት እንዲሁም ድርጅቶችና ግለሰቦች አካውንቶቻቸውን ለማስተዳደር የሚያስችላቸውን አገልግሎት በዌብሳይቱ በኩል የሚያገኙበት ነው ብሏል።
መተግበሪያው ከሚሰጣቸው አገልግሎቶች መካከል ልዩ ልዩ ሰነዶችን በዲጂታል መንገድ መፈረም አንዱ ሲሆን ፤ የአገልግሎቱ ተጠቃሚዎች የተለያዩ ስምምነቶችና ውሎችን ለማድረግ በአካል መገኘት ሳይጠበቅባቸው በሞባይል መተግበሪያው አማካኝነት የቪዲዮ ስምምነት በማድረግ በቀላሉ መፈረም እንደሚችሉ ተገልጿል፡፡
አገልግሎቱ ለድርጅቶች በተለያዩ የጥቅል አማራጮች የቀረበ ሲሆን፤ ኢትዮጵያ ለምታደርገው የዲጂታል ጉዞ ትልቅ አስተዋጾ በማድረግ ከዚህ በፊት ውልና ስምምነቶችን የመፈራረም ሂደት ይወስድ የነበረውን ጊዜ በእጅጉ እንደሚያሳጥረውና እንደሚያቀላጥፈው ተጠቁሟል፡፡::
ደንበኞች አገልግሎቱን በተለያዩ የመንግስትና የግል መስሪያ ቤቶች ይጠቀሙት ዘንድ ከሰነዶች ማረጋገጫና ምዝገባ እገልግሎቶች፤ ከኢትዮጵያ ኢሚግሬሽን፣ ከዜግነት ወሳኝ ኩነቶች ኤጀንሲ፤ ከብሄራዊ መታወቂያና ከውጪ ጉዳይ ሚኒስቴር ጋር አብሮ ለመስራት ስምምነት ላይ ተደርሷል ተብሏል።
የቪዲቸር ቴክኖሎጂ ሶልዩሽን መስራችና ስራ አስኪያጅ ኬብሮን ደጀኔ፤ "ውለታ የተሰኘው የኤሌክትሮኒክስ ፊርማ አገልግሎት፣ በኢትዮጵያ ያለውን የንግድ እንቅስቃሴ ለመለወጥና ስራችንን የበለጠ ቀልጣፋና ውጤታማ ለማድረግ አልሞ የተመሰረተ ቁልፍ ምሰሶ ነው" ብለዋል፡፡
አክለውም፤ "ይህ መተግበሪያ በመላው ኢትዮጵያ ላሉ የንግድ ተቋማትና ግለሰቦች ምቹና የተሻሻለ አገልግሎትና ቅልጥፍና እንደሚያመጣና በገበያ ላይ ከፍተኛ ተፈላጊነት እንደሚኖረው እንምናለን" ብለዋል።
ኢትዮጵያ ለመጀመሪያ ጊዜ የምትሳተፍበት የአፍሪካ ቢዝነስ ትልቁ መድረክ ነሐሴ 11 በኢስታንቡል ይከፈታል
*ከተለያዩ አህጉራት የተውጣጡ 1ሺ ኩባንያዎችና 2ሺ ልኡካን ይሳተፉበታል
*400 የኢትዮጵያ ባለሃብቶችና ነጋዴዎች በኤክስፖው ላይ እንደሚሳተፉ ታውቋል
*የተሳታፊዎች ምዝገባ ዛሬ እንደሚጀመር የመድረኩ አዘጋጆች ተናግረዋል
ኢትዮጵያ ለመጀመሪያ ጊዜ የምትሳተፍበት የአፍሪካ ቢዝነስ ፎረምና ኤክስፖ፣ በመጪው ነሐሴ 11 ቀን 2015 ዓ.ም፣ በቱርክ መዲና ኢስታንቡል እንደሚከፈት የመድረኩ አዘጋጆች አስታወቁ፡፡
ለ10ኛ ጊዜ በሚካሄደውና AFEX 2023 የሚል ስያሜ በተሰጠው በዚህ የአፍሪካ ቢዝነስ ትልቁ መድረክ ላይ ከተለያዩ አህጉራት የተውጣጡ 1ሺ ኩባንያዎችና 2ሺ ልኡካን የሚሳተፉበት ሲሆን፤ ባለሃብቶች፣ አምራቾች፣ ላኪዎችና አስመጪዎች ምርትና አገልግሎታቸውን የሚያስተዋውቁበት፣ የንግድ ትስስር የሚፈጥሩበት፣ አዳዲስ የቢዝነስ ዕድሎች የሚያፈላልጉበት እንዲሁም ልምድና ተሞክሮ የሚለዋወጡበት መድረክ እንደሚሆንም ተጠቁሟል፡፡
የአፍሪካ ቢዝነስ ፎረም አዘጋጆች በዛሬው ዕለት ረፋድ ላይ በስካይ ላይት ሆቴል ጋዜጣዊ መግለጫ ሰጥተዋል፡፡ በዚህ ጋዜጣዊ መግለጫ ላይ የህዝብ ተወካዮች ም/ቤት አባል አምባሳደር ዲና ሙፍቲን ጨምሮ ከፍተኛ የመንግሥት ሃላፊዎች፣ የንግዱ ማህበረሰብ አባላትና ታዋቂ አርቲስቶችና ግለሰቦች ተገኝተዋል፡፡
የአፍሪካ ቢዝነስ ፎረምና ኤክስፖ - AFEX 2023 ከኤግዚቢሽን በላይ ነው ያሉት የተርኪሽ አፍሪካ ቢዝነስ ማህበር (TABA) ም/ፕሬዚዳንት ሚ/ር ኢንሳሪ ኮቻክ፤ በትብብርና በአጋርነት መሥራት ከፍ ከፍ የሚደረግበትና የሚወደስበት መድረክም ነው ብለዋል፤ በጋዜጣዊ መግለጫው ላይ ባደረጉት ንግግር፡፡
ኢትዮጵያና ቱርክ ብዙ የሚያመሳስሏቸው ነገሮች እንዳላቸው የጠቆሙት የህዝብ ተወካዮች ም/ቤት አባል አምባሳደር ዲና ሙፍቲ በበኩላቸው፤ እንዲህ ያለ የቢዝነስ መድረክ ለኢትዮጵያ ባለሃብቶችና ነጋዴዎች ከሚሰጠው ከፍተኛ ጥቅም ባሻገር የሁለቱን ታላላቅ አገራት ግንኙነትና ትስስር የበለጠ እንደሚያጠናክርም ገልጸዋል፡፡
ለአፍሪካ ቢዝነስ ፎረም አዘጋጆች ምስጋናቸውን በማቅረብም፣ የቢዝነስ ኤክስፖው የተሳካ፣ የአገራቱ ግንኙነትም የሰመረ እንዲሆን ተመኝተዋል፡፡ አምባሳደሩ አያይዘው ባስተላለፉት መልዕክት፤ይሄ አገር (ኢትዮጵያን ማለታቸው ነው) ብዙ ለዓለም ያልተነገረ፣ ያልተዋወቀ ታሪክ ያለው አገር ነው ሲሉ ጥቂቶቹን ለአብነት ያህል ጠቅሰዋል፡፡
”ይሄ አገር ዕድለኛ አገር ነው፤ ታሪካዊ አገር ነው፤ነጻነቱን ጠብቆ የቆየ አገር ነው፤ የአፍሪካን አንድነት ለማምጣት ብዙ ጥረትና ትጋት ያደረገ አገር ነው፤ለአፍሪካ ሰላም የተዋደቀ አገር ነው፤“ ያሉት አምባሳደር ዲና ሙፍቲ፤ አዲሱ ትውልድ አያቶቹና አባቶቹ የሰሩትን እያደነቀና ለዓለም እያስተዋወቀ፣ “እኔስ ምን ሰራሁ?“ ብሎ ራሱን መጠየቅ እንዳለበት አሳስበዋል፡፡
በኢትዮጵያ ንግድ ሚኒስቴር የኢትዮጵያ ታምርት ፕሮጀክት አስተባባሪና የሚኒስትሩ አማካሪ አቶ አስፋው አበበ እንደተናገሩት፤ በመጪው ነሐሴ አጋማሽ በኢስታንቡል በሚካሄደው የቢዝነስ መድረክ ላይ የኢትዮጵያ ባለሃብቶችና ኢንቨስተሮች እንዲሳተፉ በማድረግ፣ ምርትና ገበያቸውን ማሳደግ እንዲችሉ እንዲሁም ከቱርክና አፍሪካ ነጋዴዎች ጋር የንግድ ትስስር የሚፈጥሩበት ዕድል ይመቻቻል፡፡ ባለሃብቶቹ ከቱርክ የተማሩትንና የቀሰሙትንም አገራቸው ላይ መጥተው እንዲሰሩበት ይደረጋል ብለዋል፤ አቶ አስፋው፡፡
የአፌክስ እና ተርኪሽ ታባ (TABA) የብራንድ አምባሳደሯ ወ/ሮ ሦስና መሠረት በሰጡት ማብራሪያ፤ የአፍሪካ ቢዝነስ ፎረምና ኤክስፖ - አፌክስ 2023 ፤ በቱርክና አፍሪካ መካከል የንግድ ዲፕሎማሲያዊና ማህበራዊ ትስስር በማድረግ፣ ከተለያዩ የዓለማችን ክፍሎች የመጡና በተለያየ ዘርፍ የተሰማሩ ድርጅቶችና ግለሰቦች የሚገናኙበት ግዙፍ መድረክ ነው፤ ብለዋል፡፡
በቢዝነሱ ዓለም አንቱ የተባሉ የንግድ ሥራ ፈጣሪዎች፣ ባለሃብቶች፣ መንግሥታዊና መንግሥታዊ ያልሆኑ ተቋማት፣ ተጽዕኖ ፈጣሪዎችና ታዋቂ ሰዎች በመድረኩ ላይ ለመታደም ኢስታንቡል ይከትማሉ ያሉት ወ/ሮ ሦስና፤ በዚህ መድረክ የተለያዩ ኩባንያዎች ግንባር ፈጥረው የንግድ ትስስሩን ወደላቀ ከፍታ ያደርሱታል ብለዋል፡፡
በአውሮፓ ከሚገኙና በግዙፍነታቸው ከሚታወቁ ኮንቬንሽን ሆቴሎች ተጠቃሽ በሆነው ፑልማን ኢስታንቡል ኮንቬንሽን ሆቴል፣ ከነሐሴ 11 እስከ ነሐሴ 13 ቀን 2015 ዓ.ም፣ ለሦስት ቀናት በሚዘልቀው የአፍሪካ ቢዝነስ ፎረም ላይ ጨርቃጨርቅ፣ ግብርና፣ ግንባታ፣ ማሽነሪ፣ ትምህርትና ጤና፣ አላቂ እቃዎችና አይሲቲን ጨምሮ 10 ዘርፎች የሚሳተፉ ሲሆን፤ ጎን ለጎንም 12 ጉባኤዎች እንደሚካሄዱ ታውቋል፡፡
በኢስታንቡል የሚካሄደው የቢዝነስ ፎረምና ኤክስፖ፣ ከሌሎች መሰል መድረኮች የሚለይባቸውን ገጽታዎች የጠቀሱት የብራንድ አምባሳደሯ፤ መድረኩ ሁሉንም በአንድ ላይ በመያዙ (ኤግዚቢሽን፣ አንድ ለአንድ ግንኙነት፣ የጠረጴዛ ዙሪያ ውይይት) እንዲሁም በኢስታንቡል የተከበረ የኮንቬንሽን ሆቴል ውስጥ የሚካሄድ መሆኑም የተለየ ያደርገዋል ብለዋል፡፡
በአፍሪካ ቢዝነስ መድረክ ላይ ለመሳተፍ 400 የኢትዮጵያ ባለሃብቶችና ነጋዴዎችን ወደ ኢስታንቡል ይዘን ለመሄድ አቅደናል ያሉት ወ/ሮ ሦስና መሠረት፤ የቢዝነስ ፎረሙ ይፋ የተደረገበት የዛሬው ጋዜጣዊ መግለጫ እንደተቋጨ የተሳታፊዎች ምዝገባ እንደሚጀምሩ አስታውቀዋል፡፡
10ኛው የአፍሪካ ቢዝነስ መድረክ የተዘጋጀው በታባ ተርኪሽ ሲሆን፤ ማህበሩ በቱርክና አፍሪካ መካከል የንግድ ትስስርን ለማጠናከር ታልሞ የተቋቋመ ነው፡፡ ማህበሩ እ.ኤ.አ ከ2010 ወዲህ 5 ትላልቅ ጉባኤዎችን፣ 50 ኹነቶችን፣ 1500 የንግድ ስምምነቶችን፣50 ኢንቨስትመንት የማቀላጠፍ ተግባሮችን፣ 90 የሁለትዮሽ ስብሰባዎችን፣ 8 የሦስትዮሽ ስብሰባዎችን ማስተባበሩ ታውቋል፡፡
የአድዋ መቶኛ ዓመት ዝክረ በዓል
በተቋም ዲሬክተርነቴ ዘመን ብዙ የደከምኩበትና ኋላም ዋጋ ያስከፈለኝ ነገር ቢኖር፣ በ1988 ዓ.ም የተደረገው የአድዋ መቶኛ ዓመት ዝክረ በዓል ነው፡፡ እኔ በዚህ የታሪክ አጋጣሚ የተቋሙ ዲሬክተር መሆኔን እንደ ትልቅ እድል ነበር የቆጠርኩት፡፡ ሙያዬንና የተቋሙን ዝናና እምቅ የመረጃ ሀብት በመጠቀም ይህን የኢትዮጵያን የሃያኛ መቶ ዓመት ዕጣ ፈንታ ከማንኛውም ጉዳይ በበለጠ የወሰነ ክስተት በማይረሳ ሁኔታ ማክበሩን ዐቢይ ተልዕኮዬ አድርሄ ተነሳሁ፡፡ ለዚህም እንዲረዳኝ የተቋሙን የዳበረ ልምድ በመከተል የብሔራዊ ዝግጅት ኮሚቴ አቋቋምኩ፡፡ በኔ ሰብሳቢነት የሚመራው ኮሜቴ አባላት የሚከተሉት ነበሩ፡- ፕሮፌሰር መርዕድ ወልደ አረጋይ፣ ፕሮፌሰር ሺፈራው በቀለ፣ ዶ/ር ካሣዬ በጋሻው ( በወቅቱ በባህል ሚኒስቴር የቅርስ ጥናትና ጥበቃ ባለስልጣን ዲሬክተር)፣ ዶ/ር ፈቃደ አዘዘ፣ አቶ አክሊሉ ይልማ (ጸሐፊ)፣ አቶ አቡበከር አብዶሽ (የተቋሙ አስተዳዳሪ)፣ አቶ ደግፌ ገብረ ጻድቅ፣ አቶ ሰሎሞን ወረደ ቃል (ከባህል ሚኒስቴር)፣ አቶ ጸጋዬ አሰፋ (ከዩኒቨርሲቲው ፋይናንስ ክፍል)፣ እና አቶ ይሁን በላይ መንግስቱ፡፡ ኮሚቴው ስራውን የጀመረው ከበዓሉ ከአንድ ዓመት ተኩል በፊት ነበር፡፡ ዋና ተግባራት አድርጎ የያዛቸውም ሦስት ነበሩ፡- በአድዋ ድል ላይ በዓይነቱ የመጀመሪያ የሆነ ትልቅ ዓለም አቀፍ ጉባኤ፣ የአድዋ ጦርነት ከመነሻው እስከ ድምዳሜው ሥዕላዊ በሆነ መንገድ የሚገልጽ ዐውደ ርዕይ እና በአማርኛና በእንግሊዝኛ የተዘጋጀ ዘጋቢ ፊልም (ዶኩሜንታሪ)፡፡
የዝክረ በዓሉ ዝግጀት ሁለት ተፃራሪ የሆኑ ተግዳሮቶች ነበሩበት፡፡ በአንድ በኩል በወቅቱ ከኢትዮጵያዊነት ይልቅ የብሄረሰብ ማንነትን መመሪው አድርጎ የተነሳው መንግስት ይህን የኢትዮጵያዊነት ስሜት የሚቀሰቅስ ዝግጅት የጎሪጥ ማየቱ ነው፡፡ በተለይም ዝግጅቱ የራሴን አቋም ያራምዱልኛል ሊላቸው በማይችላቸው ሰዎች መከናወኑ ሳይጎረብጠው አልቀረም፡፡ ስለሆነም ይመስላል የተቋሙን እንቅስቃሴ ከመደገፍ ይልቅ ብሄራዊ ኮሚቴ ብሎ ሌላ አዘጋጅ አካል ያቋቋመው፡፡ ይህም አልበቃ ብሎ ድሉ የአንድ ክልል ድል ይመስል በትግራይ ልማት ማህበር ስር አንድ ሌላ ኮሚቴ ደግሞ ተቋቋመ፡፡ ይህም ሆኖ መንግስት ለአዘጋጀው ኮሚቴውም ቢሆን ያደረገው የገንዘብ ድጋፍ ይህን ያህል የሚያመረቃ አልነበረም፡፡ መጀመሪያ ከተሰጠው የመቶ ሺህ ብር መንቀሳቀሻ ገንዘብ በላይ ተጨማሪ ስለመሰጠቱ እርግጠኛ አይደለሁም፡፡ ታሪክ በምፀት የተመላች ናትና እኔ እስከከማውቀው ድረስ ለዝግጅቱ ከፍተኛውን ገንዘብ ያዋጡት ኢትዮጵያውያን ሳይሆኑ ጣልያኖች ነበሩ፡፡ የአዲስ አበባው ጁቬንቱስ ክበብ አባላት በአንድ ምሽት ባደረጉት የገንዘብ መዋጮ ስድስት መቶ ሺ ብር ማሰባሰባቸውን አውቃለሁ፡፡ ከዚህ ውስጥ ለኛ ኮሚቴ ሳንቲም አልደረሰንም፡፡ ይህም ሆኖ እስከተቻለ ድረስ ከሁለቱ ሌሎች ኮሚቴዎች ጋር በትብብር ለመስራት ሞክረናል፡፡
በሌላ በኩል ደግሞ የአድዋ ድል በዓል አዲስ አበባ እንጂ አድዋ (ትግራይ) መከበር የለበትም የሚል ጽንፈኛ አመለካከትም ነበር፡፡ የኛ አቋም በዓሉ አዲስ አበባም አድዋም መከበር አለበት የሚል ነው፡፡ ይህን ዓይነቱን ጽንፈኛ አመለካከት በመቃወምም በጦቢያ ጋዜጣ ላይ ሰፋ ያለ ገለጻ ማድረጌን አስታውሳለሁ፡፡ ገና ለገና በስልጣን ላይ ያለው መንግስት ከትግራይ የበቀለ ነው በማለትና ከርሱ ጋር ያለን ቅራኔ በመመርኮዝ ታሪካዊዋን አድዋ ወደ ጎን ለማድረግ መሞከር ኢ-ታሪካዊ ነበር፡፡ ከሌሎች አገራት ልምድም እንደምንማረው እንዲህ ያሉ ታሪካዊ ክንዋኔዎች ሲዘከሩ ቦታው ድረስ በመሄድ ነው እንጂ እቦታው አልሄድም ብሎ በማደም አይደለም፡፡ ከዚያ በፊትም የዶጋሊ መቶኛ ዓመት ሲከበር ቦታው ድረስ በመሄድ እንደ ነበር ካስገነዘብኩ በኋላ፣ የአድዋ ድልንም በቦታው ተገኝቶ (እነዚያ ታሪካዊ ተራሮች ስር ሆኖ) ማክበር ምን ያህል የመንፈስ እርካታ እንደሚሰጥ በአጽንዖት ገለጽኩ፡፡
በተጻራሪ ወገን የነበረው አዝማሚያ ደግሞ የምኒልክን ሚና የማኮሰስ ነበር፡፡ ይህንንም የተሳሳተ አተረጓጎም ዝርዝር መረጃ በማቅረብ ማክሸፍ ነበረብኝ፡፡ ያቀረብኳቸው ማስረጃዎችም አንደኛ በኢትዮጵያ ታሪክ መቼም ታይቶ በማይታወቅ ሁኔታ ህዝቡን እንደ አንድ ሰው ለማስተባበር መቻላቸው፤ ሁለተኛ የውስጥ ችግራቸው እስኪፈታ ድረስ (በተለይም ራስ መንገሻ ዮሐንስ እስኪገቡላቸው ድረስ) በትእግስት መጠበቃቸው፤ ሦስተኛ ከኢጣልያ እንኳ ሳይቀር የጦር መሳሪያ በማሰባሰብ ሰራዊታቸውን ማደርጀታቸው፤ አራተኛ ኢጣልያ ከአጋሯ እንግሊዝ ጋር በማበር በኢትዮጵያ ላይ የጣለችውን ዲፕሎማሲያዊ ከበባ በመበጠስ የሩሲያና ፈረንሳይን አጋርነት ለማግኘት መሞከራቸው እና አምስተኛ ደግሞ የመኳንንታቸውን፣ በተለይም የባለቤታቸውን የእቴጌ ጣይቱን፣ ምክር የመስማት ችሎታቸው ነበሩ፡፡
በጉባኤው መክፈቻ ወቅት ባደረግኩት ንግግር ይህንን አላስፈላጊ የሆነ አታካራና የተጣመመ የታሪክ አተረጓጎም አስመልክቼ የሚሰማኝን ለመናገር ተገድጄ ነበር፡፡ እንዲህ ስል፡-
We are grateful to all the individuals and institutions who had confidence in us and in our program. Our appreciation is particularly enhanced when we note that the commemoration of the Adwa victory has otherwise been attended by considerable ambivalence and confusion in some circles. It remains a curious historical irony that the commemoration of such an event as Adwa, which was notable above all for its demonstration of supreme national consensus and single-mindedness, could be attended by doubt and uncertainty.
Those of us who, in the course of the preparations for the Centenary commemoration, have had the opportunity to re-live, however vicariously, the experience of our sturdy forefathers, are assailed by no doubts. Nor do we harbor any ambivalent feelings about this great event and its commemoration. For, once we manage to rise above the transient political postures of the moment, Adwa strikes us in its eternal and immutable verity -- the right to live in freedom and the duty of closing ranks when the very survival of the nation is at stake.
ይህንን ዝክረ በዓል ስናዘጋጅ ከተለያዩ ወገኖች ለተደረገልን እርዳታ ምስጋናችን እየገለፅን፣ በሌላ ወገን ግን በዓሉ በአያሌ ብዥታና ጥርጣሬ መታጀቡ በእጅጉ ያሳዝነናል፡፡ የላቀ ብሄራዊ አንድነትና ህብረት ተምሳሌት የሆነው የአድዋ ድል በጥርጣሬና ማወላወል መታጀቡ ትልቅ የታሪክ ምፀት ነው፡፡ ዝክረ በዓሉን ስናዘጋጅ በምናብም ቢሆን የአባቶቻችን ገድል እንደገና ለማየት ለቻልነው ግን እንዲህ አይነቱ ጥርጣሬ ሲያልፍም አይነካንም፡፡ ይህን ታላቅ ድል ለመዘከርም አንዳችም ማመንታት አልተሰማንም፡፡ ምክንያቱም አላፊ ከሆኑት የፖለቲካ አቋሞ ከፍ ብለን ማሰብ ከቻልን የአድዋ ቋሚና ዘመን የማይሽረው እውነታው ወለል ብሎ ይታየናል፡- በነፃነት የመኖር መብትና የአገር ህልውና አደጋ ላይ ሲወድቅ ልዩነትን ወደ ጎን አድርጎ፣ ሆ ብሎ በአንድነት መነሳት፡፡
ስለሆነም አለማቀፍ ጉባኤውን ስናዘጋጅ ይህንን ታሳቢ በማድረግ የመጀመሪያዎቹን ሦስት ቀናት አዲስ አበባ ላይ ካደረግን በኋላ ማሳረጊያውን ቀን ደግሞ አድዋ ለማድረግ ቆረጥን፡፡ ከሁሉም በፊት ግን አንገብጋቢው የገንዘብ ጉዳይ መፈታት ነበረበት፡፡ ከመንግስት ምንም አይነት ድጎማ እንደማናገኝ ካረጋገጥን በኋላ ገንዘብ ለማሰባሰብ የተለያዩ ስልቶችን ቀየስን፡፡ የመጀመሪያው የአገር ቅርስ ማህደር የሆነውንና በህዝቡ ዘንድ እምብዛም የማይታወቀውን ተቋማችንን ማስተዋወቅና እግረ መንገዳችንንም ገንዘብ ማሰባሰብ ነበር፡፡ ለዚህም “የሻይ ግብዣ” በሚል አንድ ምሽት አዘጋጅተን ታዋቂ ሰዎችን (በተለይም ባለሃብቶችን) በመጋበዝ ስለተቋሙ ሰፋ ያለ ገለፃ ካደረግንና ካስጎበኘናቸው በኋላ ለዝክረ በዓሉ ዝግጅት የእርዳታ ቃልኪዳን ሰነድ (IOU) አስፈረምን፡፡ የመጡት ሰዎች በሙሉ ማለት ይቻላል የተለያየ መጠን የገንዘብ እርዳታ ለማድረግ ቃል ገቡ፤ በቃላቸውም መሠረት ከፈሉ፡፡ ከነዚህ መካከል ከፍተኛውን መጠን (ዐስር ሺህ ብር) የከፈሉት ካፕቴን ግዛቸው ወንድይራድና ሚስተር ፓስኳሌ መሆናቸውን ሳልጠቅስ አላልፍም፡፡
ሌላው የገንዘብ ማሰባሰቢያ መንገድ ደግሞ አዲስ አበባ የሚገኙ ታሪካዊ ስፍራዎችን አድኖ የማግኘት ውድድር (Treasure Hunt) ሲሆን ገንዘቡም የሚሰበሰበው በስፖንሰርሺፕ አማካኝነት ነበር፡፡ ሃሳቡን ያመነጨው ካጠገባችን ያልተለየን ጋዜጠኛና ገጣሚ ሙሃመድ ኢድሪስ ሲሆን ከፍተኛ የሎጂስቲክ እርዳታ ያደረገልን ደግሞ በፕሬዚዳንቱ በሚስተር ግሪጎሪ አማካኝነት የሞተር ብስክሌት ፌዴሬሽን ነበር፡፡ የሙሃመድ ኢድሪስ አስተዋጽኦ በዚህም አላበቃ፡፡ የአፄ ሚኒሊክና የእቴጌ ጣይቱ ድምጽ ለመጀመሪያ ጊዜ የተቀረጸበትን ለእንግሊዟ ንግስት ቪክቶሪያ ያስተላለፉትን የሰላምታ መልእክት ቅጂ በማስመጣትና ከጀርባው ያለውን ኮሽታ ድምጽ በማጥራት የኤግዚቢሽኑ አካል ለማድረግ አብቅቶናል፡፡ ይህ ገንዘብ የማሰባሰብ ጥረት ያልወሰደን ቦታ፣ ያላሳየን ጉድ አልነበረም፡፡
አንድ የመጣልን ሀሳብ የራት ምሽት በሒልተን ሆቴል በማዘጋጀት አንድ ጥሩ ስእል ለጨረታ አቅርበን ጠቀም ያለ ገንዘብ ማሰባሰብ ነበር፡፡ ለዚህም የመረጥነው በጣም ታዋቂ የሆነውን ኢትዮጵያዊ ሰዓሊ ነበር፡፡
ስለዚህም ደጅ ለመጥናት አንድ ሦስት ሆነን ወደ ቤቱ አመራን፡፡ ዳቦና ሻይ ከጋበዘንና ስእሎቹንም እያዞረ ካስጎበኘን በኋላ የመጣንበትን ጉዳይ አስረዳነው፡፡ በነገሩ ጥቂት ካሰበ በኋላ በእንዲህ አይነት ጥያቄዎች ምን ያህል እንደተሰላቸ ገለፀልን፡፡ በተለይም ይህ የአድዋ ዝክረ በዓል ጉዳይ መንግስት በጥርጣሬ አይን የሚያየው በመሆኑ ነገር ውስጥ መግባት እንደማይፈልግ አስረግጦ ነገረን፡፡ ነገሩን የቋጨውም የግል ፍልስፍናውን በእንግሊዝኛ ቋንቋ ከሽኖ ነው፡- “When in doubt, don’t “ (“ከተጠራጠርክ አታድርግ”)፡፡ ስለሆነም ዳቦአችንን በልተን፣ የስእል አውደ ርዕዩን አይተን ባዶ እጃችንን ተመለስን፡፡
እነዚህ እንቅፋቶች ሁሉ በአሉን ከመቼውም በደመቀ ሁኔታ ከማክበር አላገደንም፡፡
ከሁሉም በፊት ማድረግ የፈለግነው 1988 ዓ.ም ሲጠባ የአድዋ ዘመቻን የሚያንጸባርቅ የቀን መቁጠሪያ አሳትመን ማውጣት ነበር፡፡ የፊት ሽፋኑን በኢትዮጵያ ባንዲራ በተከበቡ የአድዋ አርበኞች (ከምኒልክ እስከ ካዎ ጦና፣ ከጣይቱ እስከ አባ ጂፋር) ሲያጌጥ የእያንዳንዱ ወር ገፅ ደግሞ በ1888 ዓ.ም በወሩ የተከሰተ አብይ አድዋ-ነክ ክስተት ስእላዊ መግለጫ ነበረው፡፡
ለምሳሌ በመስከረም የአፄ ምኒልክ የክተት አዋጅ፣ በጥቅምት የውጫሌን ውል የሻረው የአዲስ አበባ ውል፣ በታኃሣሥ የዶጋሊ ጦርነት፣ በጥር የመቀሌ ዕርድ (ምሽግ) ከበባው፣ በየካቲት የአድዋ ጦርነት ወዘተ…፡፡
ሌላ በበአሉ መዳረሻ ያደረግነው ዝግጅት የግጥም ውድድር ነበር፡፡ ለዚህም ብዙ ተወዳዳሪዎች ቀርበው በእኛ ግምት ከሁሉም የላቀ ሆኖ ያገኘነውን ረዘም ያለ የተሻገር ሺፈራው ግጥም በአንደኝነት መርጠን በኋላም ለበአሉ በተዘጋጀው ልዩ መፅሄት ታትሞ ለንባብ በቃ፡፡
ቀደም ሲል እንደተገለፀው፣ ዋናው ዝግጅታችን በሦስት አበይት ጉዳዮች ላይ ያጠነጠነ ነበር፡፡ የመጀመሪያው በአድዋ ጦርነት (መነሾ፣ ሂደቱና ውጤቱ) ዙሪያ አለማቀፍ ጉባኤ ማሰናዳት ነበር፡፡ ለዚህም በመላ ዓለም ለናኘው የኢትዮጵያ ጥናት ማኅበረሰብ፣ ጥሪ አድርገን አበረታች መልስ አገኘን፡፡ የጥንታዊ ፅሁፎቹን ብዛት (ስድሳ ያህል) በማጤንም፣ ጉባኤው ሰኞ የካቲት 19 ቀን አዲስ አበባ ተጀምሮ ማሳረጊያው የካቲት 22 ቀን አድዋ ላይ እንዲሆን አድርገን መርሃ ግብሩን አዘጋጀን፡፡
የአዲስ አበባው ክፍል ያለ እንከን የተጠናቀቀ ሲሆን፣ የአድዋው ግን አንዳንድ እክሎች ነበሩበት፡፡ በተለይም ፕ/ር መርዕድ ጽሁፉን በሚያቀርብበት ሰአት በተቀነባበረ መልክ በእሱ ላይ የመዝመት ሁኔታ ይታይ ነበር፡፡
መርዕድ ሁልጊዜ ከትግራዋይነቱ በፊት ኢትዮጵያዊነቱን የሚያስቀድም ስለነበር ለአክራሪ ብሄርተኞች አይጥማቸውም፡፡ እንደ አጋጣሚ ውይይቱን የምመራው እኔ ስለነበርኩ፣ የዘመቻውን መሪ አደብ እንዲገዛ አድርጌ ውይይቱ በሰላም ሊጠናቀቅ ቻለ፡፡
ይህ እንግዲህ በእለቱ ያጋጠመን ሳንካ መቅድም መሆኑ ነበር፡፡ የሻይ እረፍ ሰዓት ሲደርስ በስብሰባ ወግ የትግራዩ ኮሚቴ የደገሰልንን ለማወቅ ተወካያቸውን ሻይ የተዘጋጀልን የት እንደሆነ ስጠይቀው “ከተማው ሁሉ ሻይ ቤት ነው” ብሎ ፈጽሞ ያልጠበኩትን መልስ ሰጠኝና ሻይ ታስቦ ታለፈ፡፡
ሰውየው በአጼው ዘመን የዩኒቨርሲቲው አንጋፋ መምህርና ባለስልጣን እንደመሆኑ መጠን የአካዳሚክ ጉባኤ ስነ ስርዓትን ያጣዋል ብዬ አልገመትኩም ነበር፡፡ በሌላ በኩልም በእንግዳ ተቀባይነታቸው በሚታወቁት በትግራዋያን ምድር ይህን አይነት መልስ ማግኘቴ በጣም ገረመኝ፡፡ ምሳ ሰዓት ሲደርስም እንዲሁ ምንም የተደረገልን ዝግጅት ስላልነበረ ምሳ ፍለጋ በከተማው ተሰማራን፡፡
ለተንኮሉ ደግሞ በአሉን ለማክበር ከተማይቱ ከተለያዩ የትግራይ ከተሞች በመጡ እንግዶች ተጥለቅልቃ ስለነበር በየደረስንበት ምግብ አልቆ ጠበቀን፡፡
በመጨረሻ በነፍስ የደረሱልን ቅቅል እንቁላል እያዞሩ የሚሸጡ ልጆች ነበር፡፡ የአጋጣሚው ምፀታዊ አንድምታ ወዲያው ነው የመታኝ፡፡
“ምኒልክ ተወልዶ ባያነሳ ጋሻ፤ ግብሩ እንቁላል ነበር ይኼን ጊዜ አበሻ” እያልን እየዘመርን ነበር ያደግነው፡፡ በእለቱ አድዋ ግን እንቁላል ባይደርስልን ኖሮ በጠኔ አልቀን ነበር!
***
(ከባህሩ ዘውዴ “ኅብር ሕይወቴ ግለ ታሪክ“ መጽሐፍ የተቀነጨበ)
አፈቅርሻለሁ ነፍሴ፤
አፈቅርሻለሁ ነፍሴ፤
እንደ እራሴ
እንደ አበቦቹ ሽታ፤
እንደ ቢራቢሮ እስክስታ፤
እንደ ጥርኝ ጭቃ፤
ልክ እንደ ስጦታ ዕቃ፤
እወድሻለሁ እኔ፤ እወድሻለሁኝ፡፡
እንደ ፍልስፍና ሃሳብ፤
ሊጠግብ እንዳለ ረሃብ፤
እንደ ህፃን ልጅ ሳቅ፤
እንደ ዘላለማዊ ሃቅ፤
እወድሻለሁ እኔ፤ እወድሻለሁኝ፡፡
እንደ ሎጂክ፤
እንደ ተፈጥሮ ህግ፤
እንደ ቋንቋ፤
ልክ እንደ ሙሉ ጨረቃ፤
እወድሻለሁ እኔ፤ እወድሻለሁኝ፡፡
እንደ ሙዚቃ ቅንጣት፤
እንደ አልጋ ውስጥ ትኩሳት፤
ልክ እንደ እናቴ ስም፤
እንደ ልጅነቴ ህልም፤
እወድሻለሁ እኔ፤ እወድሻለሁኝ፡፡
እንደ ግጥም ስንኝ፤
አንጀሎ እንደጠረበው ቋጥኝ፤
እንደ ጠዋት እንቅልፍ፤
እንደ አየን ራንድ ፅሁፍ፤
እወድሻለሁኝ እኔ፤ እወድሻለሁኝ፡፡
እንደ ብርቱካን ውሃ፤
እንደ ብርሃን ዘሃ፤
እጄ ላይ እንደያዝኩት ሲጋራ፤
እንደ ቀዝቀዛ ቢራ፤
እንደ ሊዮናርዶ ሥራ፤
እወድሻለሁ እኔ፤ እወድሻለሁኝ፡፡
አፈቅርሻለሁ ፍቅር፤
አፈቅርሻለሁ ነፍሴ፤
ልክ እንደ እራሴ፡፡
(አሸናፊ አሰፋ)
ነገረ ህትመት ወ መጻሕፍት
አንድ መጽሐፍ በሽያጭ ረገድ ብዙ ሺ ኮፒ ታትሞ በአንድ ሳምንት ተሽጦ ስላለቀ ብቻ በይዘቱ ምርጥ ነው ማለት አይደለም፡፡ በብዙ ሺ ኮፒ መታተሙ፣ ለመነበብ ተደራሽ ያደርገዋል እንጂ በሁለንተናው ሚዛን የሚያነሳ ብቁ ስራ ነው የሚያስብል ማረጋገጫ አይሆንም፤ ወይም ሊሆን አይችልም፡፡ (አልባሌ ሆኖ ሰፊ ተነባቢነት ያገኘ ስራ ብዙ መጥቀስ ይቻላልና) በዋናነት የመጽሐፉ ሀሳብ ለአእምሮ ብርሃን በመስጠቱ፣ ልብን በመለወጥ ብቃቱ፣ አማራጭ የኑሮ ቀዳዳዎችን አጮልቆ በማመላከቱና በሌሎችም አበይት መመዘኛዎች ሊለካ ይችላል፡፡
(ከሀገር በቀል የህትመት ቀለም ጎርፍ ውስጥ በብዛትም ሆነ በተነባቢነት ስፋት የትላንቱ ፍቅር እስከ መቃብር እና የዚህ ዘመኑ ዴርቶጋዳን እሚስተካከል ይኖር ይሆን?)
በውጭው አለም ከ1500 ዓመታት በፊት የታተሙ መጻሕፍት ዛሬ-ዛሬ አስገራሚ ዋጋን ሰቅለዋል፡፡ ለአንድ ቀደምትና ነባር መጽሐፍ ብዙ ሺህ ዶላር ማውጣት እንግዳ መሆኑ አብቅቷል፡፡ ዘመን አይሽሬ የጠፉ ቅጂ ስራዎች ከሚገመተው በላይ ብዙ እጥፍ በሆነ ገንዘብ ሊሸመቱ ያልቻሉበት ደረጃ ላይ ናቸው፡፡ በአለማችን ውስጥ ገናና ክብር ያገኙ መጻሕፍት ሆነው ነገር ግን ህትመታቸው በመጥፋቱ ብቻ ቀዳሚነቱን የወሰዱም እንዲሁ መጥቀስ ይቻላል፡፡ ጆን ስናይደር “A Guid through Book land ” በተሰኘ ተወዳጅ መጽሐፉ ለአንድ ነጠላ ህትመት ከተከፈሉ ዋጋዎች ሁሉ የላቀው ክፍያ ብሎ በጥናቱ ካካተታቸው መካከል ይሄ ይገኝበታል፡፡…በ1930 በተለምዶ የቮልቤከር ስብስቦች ተብለው የሚጠሩ መጻሕፍት በኮንግረስ ላይብረሪ ውስጥ ይገኛሉ፡፡ የአሜሪካን ኮንግረስ እኚህን የተበታተኑ ቅጂዎች ከመላው አለም ሰብስቦ ለማኖር ባሳለፈው ውሳኔ መሰረት 600,000 ዶላሮችን አውጥተውበታል፡፡ በጊዜው ለጥቂት ህትመት ከተከፈሉ ዋጋዎች ውዱ ክፍያ ነበር፡፡ ሌላው በ1485 በዌስት ሚኒስቴር ታትመው ከወደሙትና ለተረፈው ብቸኛ “Morted Arthur” ለተሰኘ መጽሐፍ ድርጅቱ 42,800 ዶላሮችን አውጥቷል፡፡ ቀደምት አብያተ መጻሕፍት በአብዛኛው በግብፅ፣ በአሶር እና በባቢሎን የሚገኙ ነበሩ፡፡ መጻሕፍቶቹ ጥንታውያን ከመሆናቸው ባሻገር ከወረቀት በፊት የሚጠቀሙበት በፓፒረስ የተሰጡ ጥቅሎች ከመሆናቸው ባለፈ፣ አንድም ከእጥረታቸው አንድም ከእድሜ ባለጠግነታቸው ጋር ተያይዞ ለዋጋቸው አለቅጥ መናርና መወደድ በተመራማሪያኑ እንደምክንያት ይጠቀሳል፡፡
ወደ አገራችን መለስ ብለን ደግሞ እንይ፡፡ ስለ መጻሕፍት ሕትመት ሲወሳ በአቢይነት ሶስት ዘርፎች ያሉ መሆናቸውን እቁጥር ውስጥ ማስገባት ያሻል፡፡ እነርሱም የመማርያ መጻሕፍት፣ የሥነጽሁፍና ጠቅላላ እውቀት ናቸው፡፡ በአጥኚዎች ዘንድ ተደጋግሞ እንደሚነገረው፤ የአፍሪካ የመጻሕፍት ሕትመት ዘጠና ከመቶ ያህሉ በመማሪያ መጻሕፍት ወይም በትምህርታዊ ሕትመት ላይ ያተኮረ ነው፡፡ በኢትዮጵያም የሚታየው ይኸው ነው፡፡ ይህም ከሥነጽሑፍ፣ ከጠቅላላ እውቀት፣ ከጋዜጣና መጽሔቶች በላቀ ሀገራቱ ለትምህርት ቅድሚያ የሚሰጡ መሆናቸውን ያመላክታል፡፡ ይህ ትኩረት አይቀሬና ሁሌም የሚኖር መሆኑ እርግጥ ነው፡፡ ይሁንና የሕትመቱ ኢንዱስትሪ በዚህ ላይ ብቻ ተወስኖ ሲያተኩር፣ የሌሎች መጻሕፍትን ሕትመት ያቀጭጫልም-ያዳክማልም ተብሎ በአጥኚዎች ዘንድ ይሰጋል፡፡ ተባባሪ ኘሮፌሰር ዘሪሁን አስፋው በጉዳዩ ላይ ከፃፉ አጥኚዎች መካከል አንዱ ናቸው፡፡ የስነጽሑፍ ምሁሩ “ከበአሉ ግርማ እስከ አዳም ረታ” በተሰኘ መጽሐፋቸው፤ “የኢትዮጵያ የመጻሕፍት ሕትመት የደረሰበት የእድገት ደረጃ፣ የታዩ ችግሮች እና መፍትሔዎች” በሚል ንዑስ ርዕስ ስር ባሰፈሩት ጥናታዊ ሀተታቸው ለአገራችን ስጋቶች ናቸው ያሏቸውን በሶስት ከፍለው እንደሚከተለው አስቀምጠዋል፡፡…“የሕትመት እንዱስትሪው በአብዛኛው በመንግስት በጀት ላይ ብቻ ይወድቃል፡፡ አልፎ-አልፎ በእርዳታ ሰጪ ድርጅቶች ወይም አገሮች በጎ ፍቃድ ይሆንና ዘላቂነቱ ያጠያይቃል፡፡ የሀገሩ መንግስት በሚያወጣው ስርዓተ ትምህርት ላይ መጻሕፍቱ ስለሚመሰረቱ የደራሲዎቻችንና የአሳታሚዎችን የፈጠራ አቅም ይገድባል፡፡ የመጻሕፍት ንግዱ በሀገሩ ላይ ብቻ ተወሰኖ ይቀርና የገበያ ስፋት እንዳይኖር ያደርጋል”፡፡(ገጽ.137)
በእርግጥ ወደ አገራችን መለስ ብለን ስናጤን ከነዚህ ስጋቶች በላይ አያሌ ችግሮች እንዳሉ ይታወቃል፡፡ ደራሲዎቻችንም ዘወትር የሚያማርሩበት ዋነኛ ተግዳሮት መሆኑ እሙን ነው፡፡ ምንም እንኳን የመማሪያ መጻሕፍት ሕትመት በዓለም ደረጃ ከፍ ያለ ቢሆንም፣ በዚያው መጠን በበለፀጉ አገሮች ያሉ አሳታሚዎች የመማሪያ መጻሕፍት ሕትመት ዋና መሰረታቸውም ሆነ ጉዳያቸው እንዳልሆነ ይጠቀሳል፡፡ ዛሬ-ዛሬ የመጻሕፍት ሕትመት ዋጋው ሰማይ ነው፡፡ ከሌሎች የኢኮኖሚ መሰረቶች አንፃር ሲታይ ለሀገር ኢኮኖሚ የሚያደርገው አስተዋጽኦ ትልቅ ላይሆን ይችላል፡፡ ነገር ግን ለዜጎች የአእምሮ ብልጽግና አስፈላጊነቱ ብሎም ያለው ጉልህ አስተዋጽኦ በጣሙን ላቅ ያለ ነው፡፡ ሀገር የተማረ እና በልቶ የሚያድር ዜጋ ብቻ ሳይሆን ያነበበና ማሰብ የሚችል ትውልድም ያስፈልጋታል፡፡ እንዲህ ያሉ ዜጎች የሚፈጠሩት ደግሞ መንግስት ከመማሪያ መጻሕፍት በላቀ በሌሎች ህትመቶች ላይ ትኩረት ሰጥቶ መስራት ሲችል ብቻ ነው፡፡ ስለዚህ ከሕትመት ጋር የተያያዙ ችግሮችን ለማቃለል ወይም ለማስቀረት በአጥኚዎች በዋነኛነት ከተሰጡ የመፍትሔ ሀሳቦች መካከል የሚከተሉት ይጠቀሳሉ፡፡ የአሳታሚዎች ማህበራት በማቋቋም ችግሮችን በጋራ መፍታት፣ የመጻሕፍት ፖሊሲ መቅረጽ፣ በእውቀት ላይ የተመሰረተና በባለሙያዎች የተደገፈ የሕትመት ስራ መስራት፣ ደራሲዎችንና አታሚዎችን፣አከፋፋዮችንና ሻጮችን…አቀራርቦ ማነጋገር የመሳሰሉት ጥቂቶቹ ናቸው፡፡ ከታሪካዊ ዳራ አንፃር ስንመለከተው አገራችን ከሌሎች የአፍሪቃ አገሮች የተሻለች እንደነበረች ጉዳዩን ያጠኑ ተመራማሪያን ጽፈዋል፡፡ ለምሳሌ አልበርት ዤራርድ በአገርኛ ቋንቋ የፈጠራ ስራዎችን በማሳተም ረገድ ከሌሎች የአፍሪቃ አገሮች ጋር ስትነፃፀር ኢትዮጵያ በተለየ ላቅ ያለ ደረጃ ላይ ናት ብለው ጽፈዋል፡፡ ይህን ያሉት ከዛሬ 41 ዓመት በፊት ነው፡፡ ይህ አነጋገር በአገር ቋንቋ የማሳተም ስራ ምን ያህል በተፈለገው ደረጃ እያደገ መጥቷል ? የሚል ጥያቄ እንዲጠየቅ ያሳስባል፡፡ የምስራቅ አፍሪካ ባህልና ታሪክ ላይ በርካታ ጥናታዊ ወረቀቶችንና መጻሕፍትን እንዳሳተሙ የሚነገርላቸው የሶሾሎጂ ምሁር የሆኑት ዶናልድ ሌቪን በአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ በሚያስተምሩበት ወቅት ኢትዮጵያን የተመለከቱ ሁለት መጻሕፍት አሳትመዋል፡፡ ከነዚህ ሁለት መጻሕፍቶቻቸው በ“Wax & Gold” (በደሳለኝ ስዩም ሰምና ወርቅ በሚል ወደ አማርኛም ተመልሷል) ውስጥ በኢትዮጵያ የህትመት ጉዳይ ላይ የታዘቡትን እንደሚከተለው አስፍረው ነበር፡፡…”መጻሕፍትን ጽፎ ማሳተም በኢትዮጵያ ዘመናዊ ምሁራን ዘንድ እንደጠቃሚ ነገር የሚታይ አይደለም፡፡ በአማርኛ የሚጻፉ ወጥ መጻሕፍት ቁጥር በአመት ከ50 አይበልጡም፡፡ በእርግጥ የህትመት ዋጋ ውድነት፣ ያልተደራጀ የገበያ እጦት፣ እንዲሁም የአሳታሚ አለመኖር ለዚህ እንደ ምክንያት ይጠቀሳል፡፡ የመጽሐፍ ንባብ ባህል ያለማድረጉ ልማድ በእርግጥ ዝም ብሎ የተፈጠረ አይደለም፡፡ የአንባብያን የግንዛቤ (የትምህርት ደረጃ) ዝቅተኛ መሆን ፣ የሂስ መድረክ አለመኖር፤ ከዚህ ቀደም የነበረው ዘመናዊ የስነጽሁፍ ታሪክና የሕትመት ሁኔታ ደካማ መሆን ጠንካራ የስነጽሁፍ ጉዞ እንዳይኖር አድርጓል፡፡ (ሰምና ወርቅ-ሌቪን IV) በዚህ በክፍል ሁለት ጽሁፌ ከፍ ሲል በምሁራን የተጠቀሱትንና የተጠቆሙትን ሌሎችም ችግሮችን መንግስት ትኩረት ሰጥቶ ይሰራባቸው ዘንድ ሀተታዬ ጥቂት መንገርና ማመላከት ከቻለ በቂ ነው፡፡ አዎ፣ በኛ አገር መጻሕፍት ለጥቂቶች ካልሆነ በስተቀር መሰረታዊ ፍላጎት አይደሉም፡፡ ለኑሮ ወሳኝና አስፈላጊ ግብአትም ሆነው አይካተቱም፡፡ ቢሆኑም እንኳን ዛሬ-ዛሬ በዋጋቸው መናር ሳቢያ ቅንጦት መሆናቸው አልቀረም፡፡ በሩቁ የሚታዩ እንጂ የማይበሉ የአይምሮ የነጠሩ ፍሬዎች መሆናቸው ገሀድ ነው፡፡
ከእንግዲህ የውጥንቅጡን አለም ማምለጫዎቻችን፣ አንብበን የምንረካባቸው፣ የምናሰላስልባቸው፣ ወደ ነፍሳችን አስጠግተን የምናቅፋቸው ሰናይ መጻሕፍት ላይኖሩን ይችላሉ፡፡ ከሞላ ጎደል ከሰዎች ለሰዎች መሆኑ ቀርቶ፣ ህዝብ ጋ በቀላሉ የሚደርሱበት ዘመን አብቅቶ… በውድ ዋጋ ተገዝተው ለሳሎን ጌጥ ብቻ እሚሆኑበት ጊዜ ሩቅ አይመስልም፡፡ መንግስት በህትመትና ወረቀት ጉዳይ ላይ እጁን ካላስረዘመ በስተቀር ህዝብ በሀገር ጉዳይ የሚቀነስ እንጂ የሚደመር ትውልድ አይሆንም፡፡ እንዲሆን መጠበቅ አንድም ታሪክን ጠንቅቆ አለማወቅ አሊያም ከታሪክ አለመማር ነው፡፡
“አንድ ለመለንገድ”
ክፍል ሁለት የጥበብ መሰናዶ
ዛሬ በሀገር ፍቅር
ይካሄዳል
በገጣሚ አስታውሰኝ ረጋሳና ጓደኞቹ የተሰናዳው “አንድ ለመንገድ” ክፍል ሁለት የኪነ-ጥበብ መሰናዶ ዛሬ ሰኔ 24 ቀን 2015 ዓ.ም ከቀኑ 11፡00 ጀምሮ በሀገር ፍቅር ቴአትር ይካሄዳል። በዕለቱ ግጥም ሙዚቃ የኮሜዲ ሥራና ሌሎችም ኪነ-ጥበባዊ መሰናዶዎች የሚቀርቡ ሲሆን ገጣሚያኑ አስታውሰኝ ረጋሳ፣ ዘውድአክሊል፣ ፌቨን ፋንጮ፣ ኮሜዲያን ምናለ ያረጋል፣ አማኑኤል የሺወንድ፣ አቤል ሀጎስ እንዳልክ አሰፋ፣ ድምጻዊያኑ ዳግም፣ ፍቅሩ (ዳኒ)፣ አክሊሉ፣ መላኩ እና አርቲስት ሰለሞን ሙሄ ስራዎቻቸውን እንደሚያቀርቡም ታውቋል። በዚህ ልዩ የኪነ-ጥበብ መሰናዶ ለመታደም የመግቢያ ዋጋው 150 ብር እንደሆነም ለማወቅ ተችሏል።
እባክሽ በቃኝ አትበይ!
የተሰበቀ የህይወት ጦር፤
ቄጠማ ሆኖ ሚቀር፤
‹‹በቃኝ!›› ያሉ እለት ነው እታለም፤
‹‹ደከምኩ!›› አትበይ! ግዴለም፡፡
አጥር አልባ ነው ህይወት፣
አጥር አልባ ነው ጎጆ፣
አጥር አልባ ነው አለም፤
አትሄጂበት መንገድ፣
አትከፍቺው በር የለም፤
‹‹በቃኝ!›› አትበይ ግዴለም፡፡
ከወነጨፍሽው ቀስት ፊት፣
ኢላማሽን ለነጠቀ፤
ሕይወት፣ ጎጆ፣
አለምሽን ባሜከላ ለጨፈቀ፤
ህይወትሽን ለህይወቱ እርካብ፣
አድርጎ ለሚመኘው፤
ሞራውን አታንብቢለት፣
ፍጹም ‹‹ደከምኩ!›› አትበዪው፡፡
የሚቧጥጥሽ ቆንጥር፣ የማያሻግርሽ ፈፋ፤
ከጀምበርሽ ጋር በርክቶ፣
ከእድሜሽ ጋር እየፋፋ፤
ቢመስል የማይገፋ፤
ቆንጥርና ፈፋው ነው፣
የተስፋሽ መቅኒ እታለም፤
ያለዚያ ህይወት ይሉት ጣእም፣
ኑሮ ይሉት ገድል የለም፡፡
‹‹በቃኝ!›› አትበይ ግዴለም፡፡
በእናትሽ!
(በድሉ ዋቅጅራ)
ደቡብ ኮሪያውያን በአንድ ሌሊት ወጣት ሆነው አደሩ!
በሰው ልጆች ታሪክ ሆኖ አያውቅም፡፡ ወደፊትም ሊሆን አይችልም፡፡ በደቡብ ኮሪያ ግን በትክክል ሆኗል፡፡ ባለፈው ረቡዕ ከ50 ሚሊዬን የሚልቁ ደቡብ ኮሪያውያን ከእንቅልፋቸው የነቁት በአንድ ወይም በሁለት ዓመት ወጣት ሆነው ነው ተብሏል፡፡ ዕድሜያቸው ጨምሮ ሳይሆን ቀንሶ ነው ራሳቸውን ያገኙት፡፡ እንዴት ቢሉ? የአገሪቱ መንግሥት በዕለቱ ዓለማቀፍ የእድሜ አቆጣጠር ሥርዓትን ተግባራዊ በማድረጉ! የደቡብ ኮሪያ ባህላዊ የእድሜ አቆጣጠር ልምድ፤ እያንዳንዱ ህፃን ሲወለድ አንድ ዓመት እንደሞላው አድርጎ የሚቆጥር ሲሆን ጃንዋሪ 1 በመጣ ቁጥር በእድሜው ላይ አንድ አመት ይጨምርበታል፡፡ ይኼ ማለት ምን ማለት መሰላችሁ? ዲሴምበር 31 የተወለደ ህፃን በቀጣዩ ቀን-ማለትም-ጃንዋሪ 1 ሁለት ዓመት ይሆነዋል፡፡ በተወለዱበት ወርና ቀን ዕድሜን ማስላት ወይም ልደትን ማክበር በደቡብ ኮሪያውያን ዘንድ እምብዛም የተለመደ አይደለም፡፡ ደቡብ ኮሪያ ባለፈው ታህሳስ ወር፣ ባህላዊውን የእድሜ አቆጣጠር ልማድ በዓለማቀፍ ሥርዓት ለመተካት የሚያስችላትን ህግ በፓርላማ ማፅደቋ ይታወቃል፡፡
ይኼን ተከትሎ፣ ባለፈው ረቡዕ፣ በመላ አገሪቱ መተግበር ጀምሯል - አዲሱ ህግ፡፡ ለዚህም ነው “ደቡብ ኮሪያውያን በአንድ ጀንበር በአንድና ሁለት ዓመት ወጣት ሆነው ከእንቅልፋቸው ነቁ” የሚለው መረጃ በስፋት የተሰራጨው፡፡ በእርግጥም የደቡብ ኮሪያውያን ባህላዊ የዕድሜ-አቆጣጠር ዘዴ፣ ሰዎችን በአንድ ወይም በሁለት ዓመት የሚያስረጅ ነው-ያለ ዕድሜያቸው ዕድሜ የሚሰጥ፡፡
በአዲሱ ህግ ደቡብ ኮሪያውያን የተፈጥሮን ህግ ጥሰው ወደ ልጅነታቸው ወይም ወጣትነታቸው ተመልሰዋል ማለት ይቻላል- በአንድ ወይም በሁለት ዓመት! እርጅናን እንጂ ወጣትነትን ማን ይጠላል? ደግሞም ያለአግባብ በህይወታቸው ላይ የተጫነባቸው እድሜ ነው የተነሳላቸው - ምስጋና ለዓለማቀፉ የእድሜ አቆጣጠር ሥርዓት ይግባውና፡፡
በነገራችን ላይ ደቡብ ኮሪያውያን ህፃን ልጅ ገና ሲወለድ አንድ ዓመቱ ነው የሚሉት ህይወቱ የሚጀምረው በእናቱ ማህፀን ውስጥ ነው ከሚል መነሻ ነው ይባላል፡፡ ጃንዋሪ 1 በመጣ ቁጥር ለሁሉም ያለ አድልዎ የሚታደለው የአንድ ዓመት እድሜ ጭማሪ ግን ተገቢ አይመስልም፡፡ የአንድ ዓመትና የሁለት ዓመት የእድሜ ልዩነት የፈጠረውም ይኼው ልማድ ነው፡፡
“ዕድሜን በማስላት ረገድ ሲፈጠሩ የቆዩ የህግ ሙግቶች፣ ቅሬታዎችና ማህበራዊ ብዥታዎች በእጅጉ እንደሚቀንሱ እንጠብቃለን” ብለዋል፤ የመንግስት ህግ አውጭ ሚኒስትር ሊ ዋን-ኪዩ ባለፈው ሰኞ ለጋዜጠኞች በሰጡት መግለጫ፡፡
በመስከረም 2022 ዓ.ም በተካሄደ የመንግስት ጥናት መሰረት፤ 86 በመቶ የሚሆኑት ደቡብ ኮሪያውያን፣ አዲሱ ህግ ተግባራዊ ሲደረግ፣ በእለት ተእለት ህይወታቸው ዓለማቀፉን እድሜ እንደሚጠቀሙ ነው የተናገሩት፡፡
“በባህላዊው የኮሪያ የእድሜ አቆጣጠር፣ በቀጣዩ ዓመት 30 ዓመት ይሆነኝ ነበር፤ በአዲሱ የእድሜ አቆጣጠር ስርዓት ግን በሁለት ዓመት ወጣት ሆኛለሁ” ብላለች፤ በሶል የቢሮ ሰራተኛ የሆነችው የ27 ዓመቷ ኢይ ሃዩን-ጂ፡፡ “ወጣት የመሆን ስሜት በጣም ድንቅ ነው፡፡ ከ30 ዓመት ዕድሜ በትንሹ የመራቅ ስሜት ተሰምቶኛል” ስትልም ኢይ አክላለች፡፡
የአገሪቱ ፕሬዚዳንት ዩን ሱክ ዬኦል፣ በምርጫ ዘመቻቸው ወቅት፣ ዓለማቀፍ እድሜን መደበኛ ማድረግ የመንግስታቸው ቁልፍ ግብ አድርገው ነበር የገለፁት-“ማህበራዊና አስተዳደራዊ ውዥንብርን” እንዲሁም የህግ ሙግቶችን የመቀነስ አስፈላጊነትን በመጥቀስ፡፡ የመንግስት ህግ አውጭ ሚኒስቴር ባለሥልጣናት ግን አዲሱ ህግ የአገሪቱ የመንግስት አገልግሎት አሰራርን ትርጉም ባለው መልኩ እንደማይለውጠው ነው የገለፁት፤ አብዛኞቹ በዓለማቀፍ ዕድሜ ላይ የተመሰረቱ ናቸውና፡፡ የ49 ዓመቷ የመዲናዋ ሶል ነዋሪ፣ ኢይ ኢዩን-ያንግ፣ አዲሱን ህግ በበጎነት ነው የተቀበለችው፡፡ ከዚህ በኋላም እድሜዋን በ50ዎቹ ውስጥ እያለች መግለፅ እንደማያስፈልጋት ተናግራለች፡፡ “ህጉ ተፈጥሮአዊ ወጣትነትን አያጎናፅፍህም፤ ከበፊቱ በአንድ ዓመት ወጣት መባል ከሚፈጥረው ጥሩ ስሜት ውጭ የምታገኘውም እውነተኛ ጥቅም የለም” ያለችው ኢዩን-ያንግ፤ “ነገር ግን ዓለማቀፋዊ ስታንዳርዱ ይኼ ከሆነ መከተሉ ምንም ክፋት የለውም” ብላለች፡፡ ሌላው የሶል ነዋሪ፣ ኦህ ሴዩንግ-ዮዩል ይሄንኑ ሃሳብ-ተጋርቷል፡፡“ወጣት መሆን ሁሌም ጥሩ ነው” ብሏል ኦህ፤ እየሳቀና ከ63 ዓመት ዕድሜ ወደ 61 ያመጣውን አዲሱን ህግ እያወደሰ፡፡
“ልደቴ ዲሴምበር 16 ነው፤ ታዲያ ተወልጄ ወር እንኳን ሳይሞላኝ የሁለት ዓመት ልጅ ሆንኩኝ” ያለው ኦህ፤ “ለዚህ ነው (ባህላዊው የእድሜ አቆጣጠር ዘዴ) ትርጉም የማይሰጠው” ብሏል፡፡በደቡብ ኮሪያ ለውትድርና አገልግሎት፣ ለት/ቤት መግቢያ እንዲሁም የአልኮል መጠጥና የሲጋራ ማጨሻ ህጋዊ ዕድሜን ለማስላት የሚያገለግል ሌላ ሥርዓት አለ፡- በዚህ ሥርዓት ሰው ሲወለድ ዕድሜው የሚጀምረው ከዜሮ ሲሆን፤ ጃንዋሪ1 በመጣ ቁጥር በእድሜው ላይ አንድ ዓመት ይጨመርበታል፡፡ (ይኸ የካላንደር ዕድሜ ተብሎ ይጠራል) የደቡብ ኮሪያ ባለስልጣናት፣ ይህ አሰራር ለጊዜው በስራ ላይ ይቆያል ብለዋል፡፡
የእድሜ ነገር በደቡብ ኮሪያ
በደቡብ ኮሪያ ሦስት ዓይነት የዕድሜ አቆጣጠር ዘዴ ይታወቃል፡፡ የደቡብ ኮሪያውያን እድሜ፣ ዓለማቀፍ ዕድሜና የካላንደር ዕድሜ ይሉታል፡፡በደቡብ ኮሪያውያን ባህላዊ የዕድሜ አቆጣጠር ዘዴ፣ ህፃን ሲወለድ በእናቱ ሆድ ውስጥ ያሳለፈው ጊዜ ስለሚቆጠር ገና ይህችን ዓለም ሲቀላቀል አንድ ዓመት ሞልቶታል ተብሎ ይታሰባል፡፡ (ዜሮ ዓመት የሚባል እድሜ የለም)
የፈረንጆች አዲስ ዓመት ጃንዋሪ 1 በመጣ ቁጥር ሁሉም ደቡብ ኮሪያዊ (ከህፃን እስከ አዋቂ) በእድሜው ላይ አንድ ዓመት ይጨምራል- በየካቲትም ይወለድ በታህሳስ ለውጥ አያመጣም፡፡
ዲሴምበር 31 የተወለደ ህፃን፤ በነጋታው ጃንዋሪ 1 ሁለት ዓመት ይሆነዋል፡፡
ሰማዕቱ ፓትርያርክ
ለመጀመሪያ ጊዜ በኢትዮጵያ ምድር፣በኢትዮጵያውያን
ጳጳሳት የተሾሙ ሁለተኛው ፓትርያርክ
የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን አስቀድሞ በቅዱስ ሐርቤ (፩ሺ፩፻፲፯-፩ሺ፩፻፶፯ ዓ.ም.) በኋላ በዐፄ ዮሐንስ ራብዓዊ (፩ሺ፰፻፷፫-፩ሺ፰፻፹፫ ዓ.ም.) ከሊቃውንቷ መካከል መርጣ ጳጳስ ለመሾም ለእስክንድርያ ቤተ ክርስቲያን ደጋግማ ያቀረበችው ጥያቄ፣ በ፳ኛው መቶ ክፍለ ዘመን መጀመሪያ አጋማሽ ላይ መልስ አግኝቷል፡፡ በዚህም መሠረት ለመጀመሪያ ጊዜ በንግሥተ ነገሥት ዘውዲቱ ዘመን በ፲፱፻፳፩ ዓ.ም. ግንቦት ፳፭ ቀን ከራስዋ ሊቃውንት መካከል አራት አበውን መርጣ ካይሮ ላይ በቅዱስ ማርቆስ ካቴድራል በብፁዕ ወቅዱስ ዮሐንስ ፲፱ኛ አንብሮተ እድ እንዲሾሙ አድርጋለች፡፡ እንዲሁም በ፩ሺ፱፻፳፪ ዓ.ም. የግብጹ ፓትርያርክ ወደ ኢትዮጵያ መጥተው ስለ ዕጨጌ ገብረ መንፈስ ቅዱስን ሳዊሮስ ጳጳስ ብለው ሾመዋቸዋል።
ይህ በዚህ እንዳለ ኢጣሊያ ኢትዮጵያን በቅኝ ግዛት ለመያዝ እንዲሁም ቤተ ክርስቲያንዋንም ካቶሊክ ለማድረግ፣ የኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ሊቃውንትንም ለማጥፋት ፲፱፻፳፰-፲፱፻፴፫ ዓ.ም. ኢጣሊያ ከአድዋ ሽንፈቱ ፵ ዓመት በኋላ በድጋሚ በኢትዮጵያ ላይ ወረራ አደረገ፡፡ በዚህም ጊዜ ብዙ አብያተ ክርስቲያናትና ቅርሳቅርሶች ተቃጠሉ፤ ንዋያተ ቅድስት ተዘረፉ፤ ጳጳሳት፣ ካህናት፣ መነኮሳትና ዲያቆናት ምእመናንም ተገደሉ፡፡
ይሁን እንጂ ቤተ ክርስቲያናችን ይህን የግፍ ዘመን በትዕግሥት አሳልፋና እንደገና ተደራጅታ ለሕዝቡ አገልግሎቷን ቀጥላለች፡፡ ከጠላት ወረራ በኋላም ቀደም ሲል ከተሾሙት አምስት ኢትዮጵያውያን ጳጳሳት መካከል ሦስቱ ከዚህ ዓለም በሞት ስለተለዩ በአንድ ጳጳስ ብቻም ብዙ መንፈሳዊ ተግባርን ማከናወን ስለማይቻል፣ እንደገና ሐምሌ ፲፰ ቀን ፲፱፻፵ ዓ.ም. ካይሮ ላይ በብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ዮሳብ ዳግማዊ አንብሮተ እድ አምስት ኢትዮጵያውያን ጳጳሳት ተሾሙ፡፡ ከሊቀ ጳጳስ ቄርሎስ ግብጻዊ ሞት በኋላም ጥር ፮ ቀን ፲፱፻፵፫ ዓ.ም. ብፁዕ አቡነ ባስልዮስ ሊቀ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ ተብለው በፓትርያርክ ዮሳብ ዳግማዊ ተሠየሙ፡፡ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን በዚህ አኳኋን ከኀይል ወደ ኀይል ከእድገት ወደ ተሻለ እድገት እየተራመደች ቆይታ ፲፱፻፶፩ ዓ.ም. ሰኔ ፳፩ ቀን ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ባስልዮስ የኢትዮጵያ የመጀመሪያው ፓትርያርክ ሆነው ተሾሙ፡፡
እነሆ ይህ ራስን ችሎ በራስ የመተዳደር መብትና ሥልጣን ሊገኝ የቻለው በግርማዊ ቀዳማዊ ዐፄ ኀይለ ሥላሴ ከፍተኛ ጥረት በቤተ ክርስቲያኒቱ ሊቃውንት ድጋፍ፣ ፍላጎትና በእስክንድርያውያንም ስምምነት መሆኑ ምን ጊዜም ታሪክ የማይረሳው እውነት ነው፡፡
ብፁዕ አቡነ ባስልዮስ ጥቅምት ፫ ቀን ፲፱፻፷፫ ዓ.ም ከዚህ ዓለም ድካም ሲያርፉ ቅዱስ ሲኖዶስ መጋቢት ፳፰ ቀን ፲፱፻፷፫ ዓ.ም ላይ ባካሄደው የፓትርያርክ ምርጫ ብፁዕ አቡነ ቴዎፍሎስ ተመረጡ፡፡
ግንቦት ፩ ቀን ፲፱፻፷፫ ዓ.ም በመንበረ ጸባኦት ቅድስት ሥላሴ ቤተ ክርስቲያን ለመጀመሪያ ጊዜ በኢትዮጵያ ምድር በኢትዮጵያውያን ጳጳሳት፣ ሊቃነ ጳጳሳት፣ ካህናት እና ምእመናን ጸሎት በተካሄደ በዓለ ሲመት ብፁዕ አቡነ ቴዎፍሎስ ሁለተኛው የኢትዮጵያ ፓትርያርክ ሆነው ተሾሙ፡፡
ብፁዕ አቡነ ቴዎፍሎስ ከድቁና እስከ ፓትርያርክነት ቤተ ክርስቲያንን በመንፈሳዊ ቅናት፣ ትጋትና ተጋድሎ እያገለገሉ በነበሩበት ወቅት በ፲፱፻፷፰ ዓ.ም ታሰሩ፤ የደርግ ሥርዓተ መንግስት ለሦስት ዓመታት አስረው ካቆዪዋቸው በኋላ በ፲፱፻፸፩ ዓ.ም በፈፀሙባቸው ኢፍትሃዊ ግድያ ሐምሌ ፯ ሰማዕት ሆኑ፡፡
ስለብፁዕነታቸውን የመንፈሳዊ ሕይወት ተጋድሎ በዝርዝር ማቅረብ የሚቻል ቢሆንም የጽሁፌ መነሻ “ቀዳማዊ ቴዎፍሎስ ፓትርያርክ” የሚለው የአቶ ታምራት አበራ መጽሐፍ አትኩሮቴ ስለሆነ በጥልቀት ገብቼ ከመዘርዘር ተቆጥቤያለሁ፡፡
“ቀዳማዊ ቴዎፍሎስ ፓትርያርክ” በሚለው ርዕስ ስያሜ አጭር ፅሁፍ ለማዘጋጀት የፈለኩበት ምክንያት የመፅሃፉን ይዘት ለመገምገም ወይም ክፍተቱን ለመሙላት ወይም ጥንካሬውን ለመናገር ሳይሆን መፅሃፉ አሁን ላነሳነው ቅዱስነታቸውን በአካል ለማናውቀው ግን ሥራቸውንና ታሪካቸውን ለምናነበው ታናናሽ የቤተ ክርስቲያን አገልጋዮች መፅሃፉ ከያዛቸው መሰረታዊ ቁም ነገሮች ውስጥ የብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ቴዎፍሎስን ታሪክና ሥራዎች ማንበብ ብቻ ሳይሆን ለዚህ ሁሉ ሥራቸው መሰረታዊ መነሻ፣ ሃይማኖታዊም ይሁን አስተዳደራዊ፣ መዋቅራዊም ይሁን ቀኖናዊ መሠረት ምንድን ነው የሚለውን ጥያቄ እንድናነሳ መንገድ ስለሰጠን ነው፡፡
እርግጥ ነው መፅሃፉ “ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ቴዎፍሎስን በጣም በቅርበት እንድናውቃቸው የሚያደርግ፣ ከስማበለው ወይም አሉታ ታሪክ ለየት ባለ መንገድ በቅርበት የሚያውቋቸው፣ አብረዋቸው የሠሩ፣ የቅርብ አማካሪዎቻቸውን መረጃ በማድረግ መጻፉ ተአማኒነቱንና ታሪካዊ ፋይዳውን ይጨምረዋል፡፡ ከዚህ በተጨማሪ ግን አሁን እኔ ቀጥዬ የማነሳቸውን ለምን እንዲህ ሆኑ፣ ለምን እንዲህ አደረጉ፣ ለምን እንዲህ ወሰኑ የሚሉ ጥያቄዎችን ከጽንሰ ሐሳባዊ መሰረት ለመዳሰስ የሚጋብዝ አቀራረብ አለው፡፡
ሰማዕታት ለምን መከራ ተቀበሉ ሲባል በጣም ቅርብ የሆነው መልስ በጣም ታማኝና ለእምነታቸው ጽኑ ስለሆኑ ነው የሚለውን እናገኝ ይሆናል፡፡ በዚሁ ሳንቆም በጥልቀት ከመረመርን ደግሞ ስለማያልፈው የመንግስተ ሰማያት ርስት ሲሉ፣ ስለ እውነተኛው የክርስቶስ ፍቅር ሲሉ፣ ስለ ትክክለኛ ኦርቶዶክሳዊ ሃይማኖታቸውና ቤተ ክርስቲያናቸው ሲሉ የሚሉ በርከት ያሉ መልሶችን እናገኛለን፡፡ ይሄም እንዲሁ ነው፤ ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ቴዎፍሎስ ለምን እንደዚህ ዘመን ተሻጋሪ ሥራዎችን በብዙ መከራዎችና እንቅፋቶች፣ ባልተደላደለ ሁኔታና በአስቸጋሪ ፈታኝ ወቅቶች፣ በአጭር ግዜ ውስጥ ሠሩ ሲባል መልሱ ሁሉንም ማሳተፉ አይቀርም፡፡ የእኔም አላማ አሁን ሁሉንም ለመመለስ ሳይሆን፣ በተለይ ለእኛ ለታናናሽ የቤተ ክርስቲያን አገልጋዮች ልዩ ትርጉም ስላለው፣ በዚሁ ጉዳይ እንድንጨነቅና እንድናስብ ለበለጠ አገልግሎትም እንድንተጋ ለማድረግ ነው፡፡
ከማንኛውም ሥራ በፊት ሐሳብ አለ፤ በተግባር የምናየው ሥራ የሐሳቡ ውጤት ነው፡፡ ሐሳብ የሌለውና ከተግባሩ ጋር ያልተገናዘበ ሥራ ምናልባት ወይ የተቀዳ ነው ወይም በግብታዊነት የሚሰራ የይስሙላ ድካም ነው፡፡ ከማንኛውም ምርጥ ተግባር ጀርባ ዕቅድ፣ ዲዛይንና መነሻ ምክንያት አለ፡፡ ያለእቅድ የተሰራ ቤት፣ ያለትልም የተዘራ ሰብል፣ ያለምህዋር የሚሄድ መርከብ መድረሻቸውም አይታወቅም፤ ሂደታቸውም ጥበብ የጎደለው ነው፡፡ ይህን ማለት የምንፈልገው የብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ቴዎፍሎስ ሥራዎች ጀርባ ለሥራው ሁሉ መነሻ አስደናቂ የሆኑ ጥበቦችና ዘመን የማይሽራቸው በኦርቶዶክሳዊ ተዋሕዶ እምነት ቀኖና፣ አስተዳደርና ዶግማ ላይ የተመሠረቱ አስተሳሰቦች እንዳሉ ለመግለጽ ነው፡፡ከሁሉ በፊት ግን የብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ቴዎፍሎስ ፓትሪያርክ የአስተዳደር ጽንሰ ሐሳብን ለማተት የሚከተሉትን መሰረታዊ መነሻዎች ማየት ተገቢ ነው፡፡
ቅዱስነታቸው ሁለተኛው ፓትሪያርክ የሆኑት በቀዳማዊ ኃይለ ሥላሴ ላይ መፈንቅለ መንግስት ከተደረገ በሁዋላ ንጉሡ በእርጅና እድሜያቸው በርከት ያሉ ተቃውሞዎች እየመጡ ተፈጥሯዊና ሰው ሰራሽ ችግሮች እየሰፋ በነበረበት ወቅት ነው፡፡ምንም እንኳን ቤተ ክርስቲያኒቱ ለመጀመሪያ ጊዜ በታሪኳ የሯስዋ የሆነ ፓትሪያርክ ከእርሳቸው በፊት ቢሾሙም አስተዳደሩ ከንጉሱ ሞግዚትነት አልወጣም፤ የታላላቆቹ አድባራትና ገዳማት ገበዞች ሹማምንት ነበሩ፡፡ ቤተ ክርስቲያኒቱ በገንዘብም ይሁን በሰው ኃይል ያላትን ሀብት ለመጠቀም የአካባቢና የማእከላዊውን የንጉሠ ነገሥቱን መብት ጠብቃ ነው፡፡ በፓትሪያርክ ሥልጣኑም ቢሆን የንጉሠ ነገሥቱ ቀጥተኛ ጣልቃ ገብነት የተከበረ ነበር፡፡የመጀመሪያው ትልቅ እርምጃ የግብጻውያንን ቀጥተኛ ጣልቃ ገብነት በሹመታቸው አስወግደዋል፡፡ በዚህም በፓትሪያርክነት ሁለተኛው ፓትሪያርክ ይሁኑ እንጅ በሃገራቸው በመሾም የመጀመሪያው ፓትሪያርክ ናቸው፡፡ በመቀጠልም በልዩ ልዩ አጋጣሚዎች ዋና ሐሳቦች የነበሩት በሳቸው ግዜ የነበረችውን ቤተ ክርስቲያን ማገልገል ብቻ ሳይሆን የወደፊቱንም የማየት ብቃት ነበራቸው (ዶ/ር አግደው ረዴ)
እነዚህን ጉዳዮች በሚገባ ለማጤን ከዚህ ቀጥሎ ያሉትንና በአቶ ታምራት መጽሐፍ ከተጠቀሱት አንጻር ብቻ እናያለን፡፡ ቅዱስነታቸው፡-
የቤተ ክርስቲያን አንድ ወጥና ማእከላዊነቱን የጠበቀ ሆኖ በየቦታ ራስ ገዝ በመሆን ኃላፊነቱን የሚወጣ አስተዳደር በሐዋሪያት ሥርዓት ላይ የተመሰረተ “የሰበካ መንፈሳዊ ጉባኤ” ሠርተዋል፤ ይህም የቤተ ክርስቲያን አስተዳደር ከማንም ሞግዚትነት የወጣ፣ ራሱን የቻለ፣ ምንም አይት አስተዳደራዊ ድርቶን (ደባልነት) የሌለው በጣም ብቁና ዘመናዊ የሆነ፣ ሁሉን አቀፍ በመሆን እንደተፈለገው መስፋትና መጥበብ የሚችል፣ ለሀብት ቁጥጥር፣ ለሰው ኃይል ሥምሪት ለመዋቅራዊ ወጥነት፣ ለአስተዳደራዊ ተጠያቂነት፣ ለሕዝባውያንና ለካህናት የቤተ ክርስቲያን ሁለንተናዊ ተሳትፎ (አሳታፊ) የሆነ ፍጹም መንፈሳዊ የሆነ መዋቅርን መሥርተዋል፡፡ የዚህ መዋቅር መሠረታዊ ጽንሰ ሐሳብ ቤተ ክርስቲያን በራሷ ብቁ የሆነች፣ የራስዋ የሆነ ሐዋሪያዊ መዋቅር ያላት፣ ከዓለማዊ አስተሳሰብ ነጻና የተደራጀች ዘመን የማይሽረው አደረጃጀት እንዳላት ከማመንና ያንንም ከመተግበር የተነሳ ነው ብዬ አምናለሁ፡፡ በተለይም ይህንኑ አደረጃጀት ወደ ተግባር ለመለወጥ የነበሩበትን ፈተናዎች በጽናት ለመለወጥ ያሳዩት ቁርጠኝነት፣ አሁን የምናየውን የቤተ ክርስቲያን አስተዳደር ለማትረፍና ቃለ ዐዋዲውን ለአራተኛ ጊዜ እንዲሻሻል ምክንያት ሆኗል፡፡
ቅዱስነታቸው ለዓለም አቀፍ ግንኙነት ልዩ ትኩረት ነበራቸው፤ አሁን እኛ በተለያየ ሁኔታ የቤተ ክርስቲያንን ዓለም አቀፍ ግንኙነት ለማሳካት ጥረት ሲደረግ ሁልጊዜ እንደ መነሻ የሚታየው የብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ቴዎፍሎስ ጥረት ነው፡፡ በእሳቸው ተሳትፎ ቤተ ክርስቲያን የበርካታ ዓለም አቀፍ ግንኙነቶች ንቁ ተሳትፎ ከመረጋገጡ ባሻገር በአንዳንዶቹ ዓለም አቀፍ ተቋማት ውስጥ የመሥራች አባል በመሆኗ በኩራት እንድንናገር አድርጎናል፡፡
ከዚህም አልፎ በተለይ በኦርቶዶክሱ ዓለም ውስጥ በነበሩት ዓለም አቀፍ ግንኙነቶች የመሪነት ወይም የአቻነት ሚና እንድትጫወት አድርገዋል፡፡
ቅዱስነታቸው ለወንጌል አገልግሎት እና ለአብነት ትምህርት ልዩ ቦታ ነበራቸው፡፡ ስብከተ ወንጌልና ሐዋሪያዊ ተልእኮ መቋቋም፣ ሐዋሪያዊ ድርጅት፣ የሬዲዮ ሥርጭት፣ የልዩ ልዩ ሕትመቶች ተጠናክሮ መኖር መሠረቱ እሳቸው ነበሩ፡፡ በዚህም ብዙ ልንል ብንችልም ዋናው ጉዳይ የቅዱስነታቸው አስተሳሰብ የቤተ ክርስቲያንን ተቀዳሚ ተልእኮ ማስቀደማቸውን ማየት ሲሆን፤ ይህም ዋናው ምንጩ ቀደም ሲል ለመግለፅ እንደተሞከረው ለቤተ ክርስቲያን ማዕከላዊ ተልእኮ የሰጡት ትኩረትና የቤተ ክርስቲያን ተልእኮ ለመንፈሳዊ ተልእኮ ቅድሚያ የሚሰጥ፣ መንፈሳዊው ተልእኮው ላይ የተመሰረተ እንዲሆን ከሰጡት ትኩረት ነው፡፡
ቅዱስነታቸው የወጣቶችን የቤተ ክርስቲያን ተሳትፎ በተመለከተ ከሰንበት ትምህርት በወቅቱ ከነበሩ የወጣት እንቅስቃሴ አንፃር በርከት ያሉ ጉዳዮችን ልንማር እንችላለን፡፡ በየቦታው የነበሩ እንቅስቃሴዎችን መዋቅራዊ በማድረግ፣ ወጣቶች በቤተ ክርስቲያን ሕይወት ውስጥ ሥርዓትና ቀኖና ጠብቀው እንዲሳተፉና በአብነት ትምህርት ቤቶች፣ በገዳማትና በገጠር አብያተ ክርስቲያናት ከሚማሩና ከሚደክሙ ወጣቶች በተጨማሪ በከተማ ያደጉ በዘመናዊ የትምህርት ተቋማት የሚማሩ ወጣቶች የቤተ ክርስቲያንን መዋቅር አውቀው፣ የቅዱሳት መጻሕፍት ሚስጥር፣ የቅዱሳንን ገድልና ድርሳናት፣ የቤተ ክርስቲያንን ታሪክ መሠረተ እምነትና ቀኖና እንዲያውቁ ለማድረግ ብዙ ደክመዋል፡፡ ውጤቱም ዛሬ በመላው ኢትዮጵያና በመላው ዓለም የተዘረጋው የሰንበት ትምህርት ቤቶች መዋቅር ነው፡፡ የዚህ ተግባር መሰረታዊ ፅንሰ ሐሳብም አንደኛው ቤተ ክርስቲያን ተተኪ ትውልድን ያለማቋረጥ እንድታፈራ፣ ያም ትውልድ መዋቅሯንና አስተዳደሯን የሚያውቅ፣ የሚጠብቅና የሚያስጠብቅ፡፡ ከቅጥሯ ሳይርቅ የሚማር እንዲሆን ለማድረግ ሲሆን በተለይ ከዘመናዊ ትምህርት ተጽዕኖ ራሱን ጠብቆ በዘመናዊውም በመንፈሳዊውም ትምህርት የበለፀገ ትውልድ ለመቅረጽ የተደረገ ነው፡፡ቅዱስነታቸው ቤተ ክርስቲያን የራሷ ገቢ እንዲኖራት፣ በልመና እንዳትተዳደር፣ በማህበራዊ ግልጋሎት ንቁ ተሳታፊ እንድትሆን የገቢ ምንጭና የልማት ተቋማትን በመገንባት ለገዳማትና ለአብነት ትምህርት ቤቶች ድጋፍ እንዲሆኑ በማድረግ ትልቅ አስተዋጽኦ አበርክተዋል፡፡ ለዚህም የቤቶች ግንባታ፣ የልዩ ልዩ የልማት ተቋማት እንደ ጎፋ ዕደ ጥበባት ያሉ የትንሣኤ ማተሚያ ቤት ያሉ ተቋማት መመሥረታቸው ነው፡፡ የዚህ ተግባር ዋና ፅንሰ ሐሳብም ቤተ ክርስቲያን ራሷን ካልቻለችና በዓለማውያን አስተሳሰብ ቅኝ ግዛት ከወደቀች፣ ግለሰቦችና ቡድኖች ወይም የዓለማዊ አስተሳሰቦችና የቁሳዊ ግንዛቤዎች ጥገኛ እንዳትሆን ለማድረግ ነው፡፡
ቅዱስነታቸው ቤተ ክርስቲያን በሀገራዊ ልማት፣ በስደተኞች፣ በማህበራዊ ግልጋሎት ቀጥተኛ ተሳታፊ እንድትሆን አድርገዋል፡፡ በዚህም ከሀገራቸው መንግስት ጋር ብቻ ሳይሆን ከዓለም አቀፍ መንግሥታዊ የሆኑ (እንደ የተባበሩት መንግሥታት)፣ መንግሥታዊ ካልሆኑ እንደ ልዩ ልዩ የበጎ አድራጎት ተቋማት ጋር ቀጥተኛ ግንኙነት እንዲኖራት በማድረግ፣ ከመንፈሳዊ ግልጋሎቷ ጎን ለጎን ማኅበራዊ ተሳትፎዋም ጉልህ እንዲሆን አድርገዋል፡፡ ለዚህም የልማትና ክርስቲያናዊ ተራድኦ ኮሚሽን የመሰሉት ተቋማት መቋቋምን ስናይ በዋናነት ግን ቤተ ክርስቲያ ባለችበት ኅብረተሰብ ውስጥ ተጽዕኖ ፈጣሪ የምትሆነው በአባላት ብዛትና ባላት ሀብት ብቻ ሳይሆን፣ በምታደርገው ታማኝነት ያለው ማኅበራዊ ተሳትፎም ጭምር መሆኑን ያሳዩ ናቸው፡፡
የቅዱስነታቸው አስተዳደራዊ የመዋቅርና የአደረጃጀት ጽንሰ ሐሳብም ከወቅቱ ጋር አብሮ የሚሔድ፣ ታዳጊና ሒደቱ በግልጽ የሚታይ፣ ተጠሪነቱና ተጠያቂነቱ በግልጽ የታወቀ፣ ከነቀፋ የራቀና ለቁጥጥርም ይሁን ለማንኛውም ግምገማ የማያሻማ፣ የሥራ ድርሻውና የሥራ ክፍሉ ተጠሪነት በግልጽ ተለይቶ የታወቀ፣ ተደራሽና ገስጋሽ የሆነ ድርብርብ ወይም ድግምግሞሽ የሌለው፣ ለዐሠራር የማያስቸግር፣ እርስ በርሱ ተደጋጋፊ፣ የቤተ ክርስቲያኒቱን ሉዓላዊና የራሱን ክብር የጠበቀ፣ መፍትሔ ሰጪነት (መፍትሔ ፈላጊነት ሳይሆን)፣ በራሱ ባለቤትነት የጸና፣ ለሙያ ትኩረት የሰጠ፣ የቤተ ክርስቲያንን መንፈሳዊም ሆነ ማኅበራዊ፣ ልማታዊና ሀገራዊ ድርሻ በአግባቡ እንድትወጣ፣ አስተዳደሯና መዋቅሯ በምንም አይነት መለኪያ አንድን ተግባርም ሆነ ኃላፊነት ለመወጣት ብቁ የሆነ ሆኖ ራሱን ከወቅታዊ ሁኔታዎች ጋር በማገናዘብ መጠንከርና ከተለዋዋጩ የዓለም መመሪያ ራሱን ጠብቆ በመንፈሳዊ ሕልውና መቆም የሚችል መዋቅርን ሠርተዋል፡፡
በአጠቃላይ የአስተዳደር መመሪያቸው የሚያሳየው ቅዱስነታቸው ያላቸውን ጥልቅ መንፈሳዊነት፣ የመንፈሳዊ አመራር ብቃትና ያላቸውን የቀኖና ዕውቀት ነው፡፡ ከዚህም ባለፈ ያላቸውን መንፈሳዊ ልምድና ዕውቀት ወደ ተግባር ለመለወጥ የሚፈጥሯቸው መንገዶችም ይህንኑ ብቃታቸውን የሚያሳይ ነው፡፡ ለማጠቃለል፤ የቅዱስነታቸው የመዋቅርና የቤተ ክርስቲያን አስተዳደርና የመዋቅር አስተሳሰብ መርሆዎች የቤተ ክርስቲያንን ማዕከላዊነት የጠበቀ፣ ለቤተ ክርስቲያን ጥቅምና እድገት ያደላ፣ የቤተ ክርስቲያንን ሉዓላዊነት ያስከበረ፣ ለስብከተ ወንጌልና ሐዋሪያዊ ተልእኮ፣ ለመንፈሳዊ ተጋድሎ የሚያደላ፣ ራስን በመቻል ላይ ያተኮረ፣ ሁለንተናዊነት፣ ሉዓላዊነት፣ አሳታፊነት ሁሉን አቀፍነት ያለው፣ ወቅታዊነት ወይም የወቅቱን የዓለምን ሁኔታ በማየት ለዓለማዊ ወይም ዘመነኛ ሞገድ የማይበገር፣ የወደፊቱን መተንበይ የሚችል፣ ፈጣንና ተደራሽ የሆነ፣ የቤተ ክርስቲያንን መንፈሳዊም ሆነ ጥበባዊ ሀብት፣ ትውፊትና ቅርስ በመጠበቅ ላይ የተመሠረተ፣ ከግል አስተሳሰብ ወይም ከግል ጥቅም የጸዳ፤ የተለየ ነው ለማለት ይቻላል፡፡
የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ራስዋን ችላ በራስዋ ፓትርያርክ መተዳደር ከጀመረችበት ጊዜ ጀምሮ ስድስት ፓትርያርኮችን ሾማለች፡፡
የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን በአሁኑ ጊዜ በሀገር ውስጥ ፶፭ አህጉረ ስብከት ያሏት ሲሆን፣ በውጭ ሀገርም ፴ የሚሆኑ አህጉረ ሰብከትን በኢየሩሳሌም፣ በካሪቢያን ደሴቶችና በላቲን አሜሪካ፣ በአሜሪካ፣ በአውሮፓ፣ በአፍሪካ፣ በካናዳና በሌሎችም አሏት፡፡ በአጠቃላይ ቅድስት ቤተ ክርስቲያን የሌለችበት የዓለም ክፍል የለም። የተከታዮችዋ ምእመናን ቍጥርም ከሀገሪቱ ከፍተኛ የሕዝብ ብዛት የያዘ ሲሆን በርካታ ገዳማት አድባራትና አብያተ ክርስቲያናት፣ ከፍተኛ የትምህርት ተቋማት እንዲኖራት መሰረት ከጣሉ የቤተ ክርስቲያን አንጋፋና የቁርጥ ቀን አባቶች መካከል ብፁዕ አቡነ ቴዎፍሎስ - ሰማዕቱ ፓትርያርክ ዋነኛው ናቸው፡፡ የሰማዕቱ የብፁዕ አባታችን በረከታቸው ረድኤት ከሁላችን ጋር ይሁን!!! አሜን፡፡
(መምህር ዳንኤል ሰይፈሚካኤል)