Administrator

Administrator


    አንዳንድ ታሪክ ሲቆይ ተረት ይመስላል፡፡
ከዕለታት አንድ ቀን እንድ የአንደኛ ደረጃ ት/ቤት ድንቅ መምህር ነበሩ፡፡ ለተማሪዎቹ የሚሰጧቸው ቋሚ ትዕዛዛት ነበሩ፡፡ ተማሪዎቹም ያከብሩዋቸውና ይወዷቸው ስለነበር ለጥ ሰጥ ብለው ትዕዛዛቱን ይቀበሉና ይተገብሩ ነበር፡፡
1ኛው ትዕዛዝ - የቤት ሥራህን አትርሳ
2ኛው ትዕዛዝ - ለሂሳብ አሰራር ቦታ ተው
3ኛው ትዕዛዝ - መልሱን ጥርት አርገህ ፃፍ
4ኛው ትዕዛዝ - አትኮርጅ
5ኛው ትዕዛዝ - ከኮረጅክ በትክክል ኮርጅ ግን መልስ ብቻ አትኮርጅ፤ አሰራሩን
በትክክል እይ፡፡ ቢያንስ ሥራውን አውቀህ ትገለብጣለህ፡፡
6ኛው ትዕዛዝ - የቅሪላ ማልፊያ (የኳስ) ጊዜህን ቀንስ፡፡ የቤት ሥራህን እንዳያዘናጋህ
አስብ፡፡
7ኛው ትዕዛዝ - ግብረገብነትን ውደድ
8ኛው ትዕዛዝ - ከክፍልህ አታርፍድ
9ኛው ትዕዛዝ - የክፍል ሥራህን ቀጥ ብለህ ሥራ
10ኛው ትዕዛዝ - እኔ ሥነግርህ አጠንጥን፤ “ፈተና ሲሰጥህ ተርትር”
11ኛው ትዕዛዝ - እናት አባትህን አክብር፡፡
*   *   *
ሀገራችን ብዙ ትዕዛዛትን ትሻለች፡፡ ትዕዛዝ አክባሪ ዜጋም ሊኖራት ይገባል፡፡ ከወሬ መላቀቅ ያስፈልጋታል፡፡ ሹም ሽር፤ የሥራ ኮንትራት መሆኑን ጠንክሮ ማስረዳት፣ መቆጣጠርና መከታተል የግድ መኖር አለበት፡፡ ሥርዓተ - አልባነት የወቅቱ አደጋ መሆኑንና ፈጦ - ገጦ መምጣቱን አስተውለን - “እናቴ ዕንቁላል ስሰርቅ ዝም ባላልሺኝ፤ በሬ ስሰርቅ ባልተያዝኩኝ” ያለውን ልጅ ማስታወስ ነው፡፡
የሥራ ባህላችንን ማጠንከር ግዴታ ነው፡፡ ግዴታችንን እንወቅ፡፡ የቤት ሥራችንን ለአፍ ወረት ብቻ አናውራ፡፡ የአሠራር ቦታ እንተው፡፡ መልሶቻችንን በግልፅ እናስቀምጥ! ህዝብ “የሥርዓት - ያለህ!” ብሎ እስኪጮህ አንጠብቅ፡፡ ትናንሽ የክፍል ሥራዎች ተጠራቅመው የአገር ችግር እስኪሆኑ ድረስ ዕድል አንስጥ፡፡
ከሁሉም በላይ ልብ መባል ያለበት የአገራችንን መላ - ችግር እንፍታ ካልን እንኳን ተጣልተን፤ ተፋቅረንና ተቧድነንም በቀላሉ የምንገላገለው እንዳይደለ ነው፡፡ ብዙዎች ከውጪ አገር ወደ ኢትዮጵያ እየገቡ መሆናቸውን አይተናል፡፡ ይሄ አንድ ሁነኛ ነገር ነው፡፡ ብዙ ይጠበቅባቸዋል፡፡ አንድ ፀሐፊ እንዳለው፤ “ኢትዮጵያ ውስጥ እያንዳንዱ ተቃዋሚ እኪሱ ውስጥ ትንሽ ዘውድ ይዞ የሚዞር ነው፡፡ መቼ እንደምነግሥ አይታወቅም ባይ ነው!” ነገሩ ግን የመንገሥ ጣጣ ሳይሆን የሀገሪቱን ችግሮች አውጠንጥኖ ማወቅና አልጋ ባልጋ አለመሆኑን ተገንዝቦ መክሮ፣ ዘክሮ፣ ተቀናጅቶ፣ በጠላትነት ሳይፈራረጁ፤ ቅራኔ አፈታት አውቆ፤ ሽንፈትንም ድልንም ተቀብሎ መጓዝን መገንዘብ ነው፡፡ ዛሬ ዳር ቆሞ ተመልካች የማትፈልግ አገር ዘንድ እየደረስን ነው፡፡ ድርሻዬን እንዴት ላዋጣ? ከማለት ጀምሮ፣ እንዴት በአንድ ልብ እንሥራ? አንድ ትልቅ የአገር ጉዳይ ውጤት ባለው መልክ ዳር ለማድረስ አንዱ እየታገለ፣ ሌላው ዳተኛ እየሆነ፣ ፍሬ እናፈራለን ብሎ ማሰብ ዘበት ነው! የግድ ሀቀኛ ተዋናይ ሆኖ መድረኩ ላይ መገኘትን ይጠይቃል፡፡ ውሃ ዋና፤ ዳር ቆሞ አይሳካም፡፡ ያም ብርቱ ድካምን ይጠይቃል!   
የሁሉንም ተሳትፎ በሚሻ መልኩ የሁሉንም ርብርብ የሚፈለግበት ጊዜ ነው፡፡ አለበለዚያ፤ “አዳመጠች አረገዘችን አይሆንም” የሚለውን የአባቶች ብሒል መዘንጋት ነው!  



   ብዙ ሰዎች Fungal Infection በመባል በሚታወቀው የኢንፌክሽን አይነት ይጠቃሉ። መነሻችን ከብልት ጋር በተያያዘ ያለውን ሁኔታ ለማየት ቢሆንም ሰዎች ይህ ኢንፌክሽን ወይንም የሰውነት መመረዝ የሚደርስባቸው በተለያዩ የሰውነት ክፍሎች ላይ ነው፡፡ ከላይ የምትመለከቱት በፊትና በምላስ ላይ በምን መልክ እንደሚወጣ ነው፡፡ በሺዎች ከሚቆጠሩ የፈንገስ አይነቶችም ጥቂቶቹ ናቸው ሰውን ለሕመም የሚዳርጉት፡፡ ብዙ ሰዎች ደግሞ በተፈጥሮ የበሽታ መቋቋም ኃይላቸው ጠንካራ ስለሚሆን በዚህ በሽታ አይጠቁም፡፡ ለምሳሌም በሕክምና ያልታገዘ የኤችአይቪ ኢንፌክሽን ያለበት ሰው ወይም የካንሰር ሕመም ላለባቸው ሰዎች የሚሰጠው እንደ ኬሞቴራፒ ያለው ሕክምና የበሽታ መቋቋም ኃይልን ሊፈታተን ይችላል፡፡ ለረጅም ጊዜ የሚወሰድ የበሽታ መከላከያ መድሀኒቶች (antibiotics) ለሕመሙ ለመጋለጥ ምቹ ሁኔታን ይፈጥራሉ ተብሎ ይታሰባል፡፡ ባጠቃላይም የፈንገስ ኢንፌክሽን በተለያዩ የሰውነት ክፍሎች ላይ እንደሚወጣ መረጃዎች ይጠቁማሉ፡፡
በእግር ላይ የሚወጣ ፈንገስ፤ ይህ የፈንገስ አይነት Tinea Pedis በመባል ይታወቃል፡፡
ሌላው ቀይ ወይንም ብርማ መልክ ያለው በሰውት ላይ የተጉረበረበ ምልክት የሚያሳይ ነው፡፡ ባብዛኛውም ክብ ቅርጽ የሚይዝ ነው፡፡
በጭንቅላት ወይንም በራስ ቅል ላይ የሚታየው በሳይንሳዊ አጠራሩም Tinea Capitis  ይባላል፡፡
Onychomycosis የተሰኘው የፈንገስ ኢንፌክሽን የሚታየው በአብዛኛው በእግር አውራ ጣት ላይ ወይንም ሌላው የእግር አካል ላይ እንዲሁም በሌሎች ጣቶች ጥፍሮች ላይ ነው፡፡ ይህ በመራመድ ወይንም በመጫማት ጊዜ ሕመም ሊኖረው ወይንም ምቾት ሊያሳጣ ይችላል፡፡
Tinea Versicolor  የተሰኘው ደግሞ ከሌላው የአካል ክፍል ቀለምን ለየት በማድረግ በትናንሽ ክቦች በተለያዩ የሰውነት አካላት ላይ የሚታይ የፈንገስ ኢንፌክሽን ነው፡፡ ጠቆር ወይንም ደብዘዝ፤ ቀይ ወይንም ፒንክ እንደሚባለው ቀለም ባለ መልክ ከሌላው የቆዳ ክፍል ቀለም ሊለይ ይችላል፡፡
ብዙ ጊዜ ሙቀት ባለው ወይንም እርጥበት በሚሰማው የሰውነት ክፍል ሊፈጠር የሚችለው ደግሞ በሳይንሳዊ አጠራሩ Cutaneous Candidiasis ነው፡፡ ይህ አይነቱ ኢንፌክሽን ከተለያዩ ሕክምናዎች ወይንም ውፍረት ፤የስኩዋር ሕመም፤በመሳሰሉት ሁሉ ሊከሰት የሚችል በየትኛውም የቆዳ ክፍል ሊከሰት የሚችል ነው፡፡
ከላይ የተገለጸው ይህ የኢንፌክሽን ሕመም በቆዳ ላይ ብቻ ሳይሆን በአፍ በጉሮሮ አካባቢ እንዲሁም ሴቶች በብልታቸው እንደሚከሰትባቸው እሙን ነው። ሴቶች በአብዛኛው ማለትም እስከ 75% የሚሆኑት በሕይወት ዘመናቸው በብልት አካባቢ የሚፈጠር ኢንፌክሽን ያጋጥማ ቸዋል፡፡ ጥናቶች እንደሚጠቁሙት ወደ 90% የሚሆኑት ኢንፌክሽኖች የሚፈጠሩት ደግሞ በሳይንሳዊ አጠራሩ Candida albicans በሚባለው ዝርያ አማካኝነት ነው፡፡ በእርግጥ ከ20-50% የሚሆኑት ሴቶች በተፈጥ ሮአቸው ይህ Candida የተሰኘው በተፈጥሮ በብልታቸው የሚገኝ መሆኑም ጥናቶች ያረጋግጣሉ፡፡ጤናማ የሆነ ብልት ባክቴሪያ (Bacteria) እና (Yeast) ይስት እንደሚኖረው እሙን ነው፡፡ ነገር ግን   ለኢንፌክሽን መፈጠር በብልት አካባቢ የሚ ኖረው ባክቴሪያ (Bacteria) እና (Yeast) ይስት በመባል የሚጠሩት መጠናቸው ሲዛባ በተለይም (Yeast) የይስት ህዋስ በእጥፍ ስለሚባዛ ችግሩ ይፈጠራል፡፡ በእርግጥ ይህ የኢንፌክሽን አይነት ምንም እንኩዋን በግብረስጋ ግንኙነት ምክንያት መተላለፍ ቢችልም ነገር ግን በግብረስጋ ግን ኙነት  ምክንያት ከሚተላለፉ በሽታዎች ውስጥ የሚመደብ አይደለም። ይህ የኢንፌክሽን አይ ነት በማንኛዋም ሴት ብልት ሊከሰት የሚችል ነው፡፡
የፈንገስ ኢንፌክሽን ለመከሰቱ የሚታዩ ምልክቶች፤
በወሲብ ግንኙነት ወቅት የህመም ስሜት፤
ሽንት ሲሸና ሕመም ወይንም ማቃጠል፤
ከብልት ውስጥ ወፈር ያለ ወደ ግራጫ የሚወስደው እና መጥፎ ጠረን ያለው ፈሳሽ ካለ የኢንፌክሽን ምልክት ሊሆን ይችላል፡፡
የማሳከክ፤ የመቅላት ወይንም የመጉረብረብ…መልክ ካለ ኢንፌክሽን ተፈጥሮአል ማለት ነው፡፡
ብልት ለኢንፌክሽን ከሚጋለጥባቸው ምክንያቶች የሚከተሉት ይገኙበታል፡፡
በብልት ውስጥ መገኘት የሚገባው የባክቴሪያ መጠን ሲቀንስ፤
እርግዝና፤
የህክምና ክትትል የማይደረግበት የስኩዋር ሕመም፤
የሰውነት የበሽታ መከላከል አቅም መቀነስ ፤
የተሟላ አመጋገብ አለመኖር፤
የሆርሞን መጠን መዛባት፤
ጭንቀት፤
የእንቅልፍ እጦት፤
የመሳሰሉት ለዚህ ኢንፌክሽን መፈጠር ምክንያት ይሆናል፡፡ ሆኖም ግን ይህ ሕመም በቀላሉ ሊታከም እና ሊድን የሚችል ነው፡፡
በሴቶች ብልት የኢንፌክሽን ሕመም ከ4/ሴቶች ሶስቱ ያህል በሕይወት ዘመናቸው የመያዝ አጋጣሚው አላቸው፡፡ አብዛኞቹ ቢያንስ ቢያንስ ለሁለት ያህል ጊዜ ሊታመሙ ይችላል፡፡ ከዚህ በተለየ በአንድ አመት ጊዜ ውስጥ ወደ አራት ጊዜ የታመሙ ሰዎች ካሉ ግን ተከታታይ የሆነ የህክምና እርዳታ እደሚያስፈልጋቸው መረጃዎች ይጠቁማሉ፡፡
ኢንፌክሽኑን መከላከል ይቻላል፡፡
የተመጣጠነ ምግብ መመገብ፤
እርጎ በተ ጨማሪም ምግብን የሚረዱ እንደ ቫይታሚን ቢ ኮምፕሌክ ያሉትን መውሰድ፤
ልብስን በተመለከተም ከጥጥ የተሰሩ ወይንም ሐርነት ያላቸውን ልብሶች መልበስ
የውስጥ ሱሪን ሞቅ ባለ ውሀ ማጠብ፤
ከጥቅም ላይ የዋሉ የሴት ልብሶችን በቅርብ ጊዜ ወይንም በፍጥነት መተካትወይንም መለወጥ ያስፈልጋል፡፡
ማስወገድ የሚገቡ ነገሮች፤
እንደታይት የመሳሰሉ ሰውነትን የሚያጠብቁ እና ላስቲክነት ያላቸውን ልብሶች አለመጠቀም፤
እንደ ሽቶ ወይንም ጠረን መለወጫ የመሳሰሉ ኬሚካሎችን በብልት አካባቢ መጠቀምን ማቆም፤
ገላ በመታጠብ ጊዜ  ባጠቃላይ በብልት አካባቢ እርጥብ ልብስን ከውስጥ ለብሶ መቀመጥን ማስወገድ፤
የፈላ ውሀ ውስጥ መቀመጥ ወይንም መዘፍዘፍ ወይንም በተቀራረበ ሁኔታ ሙቀት ባለው መታጠቢያ ከመታጠብ መቆጠብ፤
ከላይ የተጠቀሱትን ድርጊቶች በመፈጸም ኢንፌክሽኑን አስቀድሞውኑ መከላከል ይቻላል፡፡

  የአሸባሪው ቡድን አይሲስ ታጣቂዎች በሰሜን ምስራቅ ሶማሊያ በምትገኘው የፑንትላንድ ግዛት አካባቢዎች በሚንቀሳቀሱ ነጋዴዎችና ኩባንያዎች ላይ ከፍተኛ ቀረጥ መጣላቸውን ቢቢሲ ዘግቧል፡፡
የአይሲስ ታጣቂዎች በአካባቢው በንግድ ስራ ላይ ለተሰማሩ ግለሰቦችና ኩባንያዎች በላኩት አጭር የሞባይል የጽሁፍ መልዕክት፣ “ለቡድኑ በቋሚነት ቀረጥ የማትከፍሉ ከሆነ፣ ለመሞት ዝግጁ ሁኑ” የሚል ማስፈራሪያ መስጠታቸውን ዘገባው አመልክቷል፡፡ አይሲስ ቀረጡን የጣለው በሶማሊያ አንዳንድ አካባቢዎች ተመሳሳይ ቀረጥ በመጣል ገቢ ከሚያገኘው ተቀናቃኙ የአሸባሪ ቡድን አልሻባብ የወሰደውን ልምድ ተመርኩዞ ሳይሆን አይቀርም ያለው ዘገባው፤ አይሲስ በደቡባዊ ሶማሊያ መንግስት ጦር ላይ የሚፈጽመውን ጥቃት እያጠናከረ መምጣቱንና ከአልሻባብ ጋር የነበረው ግጭት እየተባባሰ እንደሚገኝም አመልክቷል፡፡

 ጆርጅ ክሉኒ በ239 ሚሊዮን ዶላር ገቢ ቀዳሚነቱን ይዟል

    ታዋቂው ፎርብስ መጽሄት በአመቱ ከፍተኛ ገቢ ያገኙ የአለማችን ወንድ የፊልም ተዋንያንን ዝርዝር ሰሞኑን ይፋ ያደረገ ሲሆን፣ የ57 አመቱ የሆሊውድ ኮከብ ጆርጅ ክሉኒ በ12 ወራት ጊዜ ውስጥ 239 ሚሊዮን ዶላር ገቢ በማግኘት ቀዳሚነቱን ይዟል፡፡
ዋይኔ ጆንሰን በ124 ሚሊዮን ዶላር አመታዊ ገቢ ሁለተኛ ደረጃን ሲይዝ፣ የአቬንጀርሱ ተዋናይ ሮበርት ዳውኒ ጁኒየር በ81 ሚሊዮን ዶላር ሶስተኛ ደረጃ ላይ መቀመጡን ፎርብስ አስታውቋል፡፡
ክሪስ ሄምስዎርዝ በ64.5 ሚሊዮን ዶላር፣ የቻይናው ኮከብ ተዋናይ ጃኪ ቻን በ45.5 ሚሊዮን ዶላር፣ አሜሪካዊው ዊል ስሚዝ በ42 ሚሊዮን ዶላር እንደ ቅደም ተከተላቸው ከአራተኛ እስከ ስድስተኛ ደረጃን ይዘዋል፡፡
በአመቱ ከፍተኛ ገቢ በማግኘት ከአንደኛ እስከ አስረኛ ያለውን ደረጃ የያዙት የፊልም ተዋንያን በድምሩ ከግብር በፊት 748.5 ሚሊዮን ዶላር ማግኘታቸው ተነግሯል፡፡

 አውሮፕላን ማረፊያው በሙጋቤ ስም መጠራቱ እንዲቀር ተጠይቋል


    በቅርቡ የተካሄደውና ፕሬዚዳንት ኤመርሰን ምናንጋዋ ያሸነፉበት የዚምባቡዌ ምርጫ የተጭበረበረ ነው፣ ሊሰረዝ ይገባል በሚል በአገሪቱ ተቃዋሚ ፓርቲዎች የተመሰረተውን ክስ ሲመረምር የቆየው ህገ መንግስታዊ ፍርድ ቤት ክሱን ውድቅ በማድረግ የምርጫ ውጤቱን አጽድቋል፡፡
በፕሬዚዳንታዊ ምርጫው 44.3 በመቶ ድምጽ በማግኘት ሳይመረጡ የቀሩት ሙቭመንት ፎር ዲሞክራቲክ ቼንጅ የተባለው የአገሪቱ ተቃዋሚ ፓርቲ መሪ ኔልሰን ቻሚሳ፣ የአገሪቱ የምርጫ ኮሚሽን የድምጽ አሰጣጡን ያለአግባብ በማከናወን ምናንግዋ እንዲያሸንፉ አስችሏል ሲሉ ክስ መስርተው ነበር፡፡
የፓርቲው ደጋፊዎች የምርጫ ውጤቱ ይፋ መደረጉን ተከትሎ አደባባይ ወጥተው ተቃውሞ ማሰማታቸውንና ከፖሊስ ጋር ግጭት ተፈጥሮ ስድስት ሰዎች ለህልፈተ ህይወት መዳረጋቸውንም ዘገባው አስታውሷል፡፡ ባለፈው ሃምሌ ወር መጨረሻ ላይ የተካሄደው የአገሪቱ ፕሬዚዳንታዊ ምርጫ፣ ዚምባዌ ከ37 አመታት በላይ የገዟት ሮበርት ሙጋቤ ባልተወዳደሩበት ለመጀመሪያ ጊዜ ፕሬዚዳንቷን ያስመረጠችበት ምርጫ ነው፡፡
በተያያዘ ዜናም የዚምባቡዌ የቀድሞ የጦር ሃይል አባላት የአገሪቱ አለማቀፍ አውሮፕላን ጣቢያ በቀድሞው ፕሬዚዳንት ሮበርት ሙጋቤ ስም መጠራቱን እንዲያቆም መጠየቃቸውን ቢቢሲ ዘግቧል፡፡ የጦር ሃይል አባላቱ የሮበርት ሙጋቤ ስም ከአውሮፕላን ማረፊያ ጣቢያ እንዲነሳና የሌሎች ታላላቅ የአገሪቱ ባለውለታዎችና ጀግኖች ስም እንዲተካ የሚጠይቅ የድጋፍ ድምጽ አሰባስበው ለአዲሱ ፕሬዚዳንት ኤመርሰን ምናንግዋ ለማስገባት እየተዘጋጁ ነው ተብሏል፡፡
ለረጅም አመታት ሃራሬ አለማቀፍ አውሮፕላን ማረፊያ ጣቢያ በሚል ስያሜ ሲጠራ የኖረው አውሮፕላን ማረፊያ ጣቢያው፣ ባለፈው አመት ሙጋቤ ስልጣን ሊለቁ ጥቂት ሳምንታት ሲቀራቸው ስያሜው ወደ ሮበርት ጋብሬል ሙጋቤ እንዲቀየር መደረጉን ያስታወሰው ዘገባው፤”ስማቸውን ዘላለማዊ የማድረግ ጥማት ባለባቸው ሙጋቤ የተወሰደው የስም ለውጥ እርምጃ ተገቢ አይደለምና ስያሜው ይቀየርልን” ሲሉ የጦር ሃይሉ አባላት መቃወማቸውን አመልክቷል፡፡


 በደቡብ ሱዳን ላለፉት አምስት አመታት የዘለቀውን የእርስ በእርስ ግጭት በድርድር ለመፍታት ደጋግመው ሲሰበሰቡና ባለመስማማት ሲለያዩ የኖሩት የአገሪቱ ተቀናቃኝ ሃይሎች፣ ከነገ በስቲያ ሰኞ የመጨረሻውን የሰላም ስምምነት ይፈራረማሉ ተብሎ እንደሚጠበቅ ዥንዋ ዘግቧል፡፡
ተቀናቃኝ ሃይሎቹ በሰኔ ወር በሱዳን መዲና ካርቱም የሰላም ስምምነት መፈራረማቸውንና ከሁለት ሳምንታት በፊትም ስልጣን ለመጋራት ስምምነት ላይ መድረሳቸውን ያስታወሰው ዘገባው፤ ሶስተኛውንና የመጨረሻውን ስምምነት በመጪው ሰኞ ለመፈራረም ቀጠሮ መያዛቸውን አመልክቷል፡፡
ቀጣዩ ስምምነት ባለፉት ሁለት ስምምነቶች እልባት ባልተሰጣቸውና በእንጥልጥል ላይ በሚገኙ ቁልፍ ጉዳዮች ላይ መግባባት ላይ የሚደረስበትና በአገሪቱ ሰላምን ለማስፈን ተስፋ የተጣለበት እንደሆነም ተነግሯል፡፡
ባለፉት ስምምነቶች መግባባት ላይ ባልተዳረሰባቸው የስልጣን መጋራትና የግዛቶች ድንበር አከላለልን የመሳሰሉ ቁልፍ ጉዳዮችን በውይይት ለመፍታት በተቀናቃኝ ሃይሎቹ መካከል የተደረጉ ጥረቶች ተስፋ ሰጪ እንደሆኑ መነገሩን የጠቆመው ዘገባው፤ የምክትል ፕሬዚዳንቱን ስልጣን በመሳሰሉ አከራካሪ ጉዳዮች ላይም መግባባት ላይ መደረሱን አመልክቷል፡፡

 በተባበሩት መንግስታት የሚደገፈው የሊቢያ መንግስት በህገ-ወጥ መንገድ ወደ አገሪቱ የገቡ ከ700 ሺህ በላይ የተለያዩ አገራት ስደተኞችን በቀጣይነት በግዛቱ ውስጥ የማስፈር ግዴታ እንደሌለበት በመግለጽ፣ ስደተኞቹ ወደየ አገራቸው መመለስ አለባቸው ሲል አቋሙን ማስታወቁን ዥንዋ ዘግቧል፡፡
ሊቢያ ከፍተኛ ቁጥር ያላቸውን የተለያዩ አገራት ስደተኞች በግዛቷ እንድታሰፍር በተመድ የቀረበው ሃሳብ ኢ-ፍትሃዊ ነው፤ ስደተኞቹ ወደየመጡበት መመለስ አለባቸው ሲሉ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሩ ሞሃመድ ሳያላ ባለፈው ረቡዕ በሰጡት መግለጫ አስታውቀዋል፡፡
የስደተኞች መተላለፊያ በመሆን ከፍተኛ መስዋዕትነት ስትከፍል የኖረቺው ሊቢያ፣ ስደተኞችን በግዛቷ የምታሰፍርበት ሁኔታ ላይ አይደለችም ያሉት ሚኒስትሩ፤አለማቀፉ ማህበረሰብ የአገራት መንግስታት በሊቢያ የሚገኙ ስደተኛ ዜጎቻቸውን መልሰው እንዲወስዱ ጫና ማድረግ ይገባቸዋል ሲሉም ተናግረዋል፡፡ በሊቢያ የሚገኙ የስደተኞች ጊዜያዊ መጠለያ ጣቢያዎች ድንበር አቋርጠው በሜዲትራኒያን ባህር በኩል በጀልባ ወደ አውሮፓ አገራት ለመግባት ሲሞክሩ በፖሊስ ቁጥጥር ስር በዋሉና ከአሰቃቂ የባህር ላይ አደጋዎች በተረፉ በሺዎች የሚቆጠሩ የተለያዩ አገራት ህገወጥ ስደተኞች ተጨናንቀው እንደሚገኙ የጠቆመው ዘገባው፤ ስደተኞቹ በአፋጣኝ ወደ አገሮቻቸው ካልተመለሱ ከፍተኛ ቀውስ ሊፈጠር እንደሚችል መሰጋቱንም አክሎ ገልጧል፡፡


 ሚዩዚክ ሜይዴይ ከኢትዮጵስ ኮሌጅ ጋር በመተባበር በክፍሉ ታደሰ “ኢትዮጵያ ሆይ ቅፅ 2” መፅሐፍ ላይ ነገ ከቀኑ 8፡00 ጀምሮ በብሔራዊ ቤተ መፃሕፍትና ቤተ መዛግብት ኤጀንሲ አዳራሽ ውይይት ያካሂዳል፡፡ ለውይይቱ የመነሻ ሀሳብ የሚያቀርቡት የአሀዱ ሬዲዮ ዋና ሥራ አስኪያጅ፣ አርታኢና ጋዜጠኛ ጥበቡ በለጠና አቶ ኩራባቸው ሸዋረጋ ሲሆኑ መድረኩ በመምህር ሰለሞን ተሰማ ጂ እንደሚመራም ታውቋል፡፡ ፍላጎት ያለው በውይይቱ ላይ እንዲሳተፍ ሚዩዚክ ሜይዴይ ጋብዟል፡፡

 የዛሬ ሳምንት ቦሌ በሚገኘው የአክሰስ ሪል እስቴት ጽ/ቤት፣ ቤት ገዢዎች ያሰሙት የነበረው ጩኸት፣ በደል ደርሶባቸው ሳይሆን የቅርብ ዘመድ የሞተባቸው ያህል አዝነው ነበር፡፡
ጩኸታቸውን ማሰማት የፈለጉት በሰላማዊ ሰልፍ እንጂ በጋዜጣዊ መግለጫ አልነበረም፡፡ የሰላማዊ ሰልፍ ፈቃድ ሰጪው ክፍል “እስከ ዛሬ ታግላችኋል፤ አሁንም በትዕግስት መልዕክታችሁን ለሚመለከታቸው የመንግሥት መዋቅሮች አሰሙ፡፡…” በማለት በለገሳቸው ምክር ተስማምተው፣ ሰላማዊ ሰልፍ የማካሄድ ሕገ መንግሥታዊ መብታቸውን ትተው፣ ጋዜጣዊ መግለጫ ለመስጠት መገደዳቸውን፣ የአክሰስ ሪል እስቴት ቤት ገዢዎች ኮሚቴ ሰብሳቢ፣ አቶ አክሎግ ስዩም ተናግረዋል፡፡  
“በሪል እስቴት የዜጎች መዘረፍ በእኛ ይብቃ! ሀገር ከሌቦች ፀድታ ትልማ! መንግሥትና ሕግ ባለበት አገር፣ ቤት ገዢዎች ተዘርፈናል፤ ሌቦች በዘረፉት ገንዘብ ፍትህ አዛብተዋል፣…” በሚሉ መፈክሮች ታጅቦ በተጀመረው ስብሰባ፣ ጠቅላይ ሚ/ር ዐቢይ አህመድ ለሚመሩት መንግሥት ባቀረቡት ጥያቄ፤ “በ50ሺ ብር ካፒታል መኖርያ ቤት ሰርቼ አቀርባለሁ” በማለት በአገር ውስጥና በውጭ ከሚኖሩ ኢትዮጵያውያንና ትውልደ ኢትዮጵያውያን ከ1.4 ቢሊዮን ብር በላይ ሰብስቦ፣ በ6 ዓመት ውስጥ አንድም ቤት ሰርቶ አለማስረከብ፣ ግልጽ ሌብነት ነው ብለዋል፡፡
አክሰስ ሪል እስቴት በተመሰረተ በአምስተኛው ዓመት፣ የድርጅቱ መስራች፣ የቦርድ ሊቀመንበርና ዋና ሥራ አስኪያጅ የነበሩት አቶ ኤርሚያስ ታጠቅ አመልጋ፤ በድርጅቱ ሳጥን ውስጥ 129 ብር ብቻ ሲቀር አገር ጥለው በመኮብለላቸው፣ ቤት ገዢዎች፣ የደረሰባቸውን ግፍና በደል ለሚመለከታቸው የመንግሥት አካላትና ለቀድሞ ጠቅላይ ሚ/ር ኃይለማርያም ደሳለኝ ማቅረባቸውን አስታውሰዋል፡፡   አቤቱታቸውን ለጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለማርያም ደሳለኝ ጽ/ቤት አቅርበው፣ ጽ/ቤቱም የተፈጠረውን ችግር እንዲፈታና ችግሩን ከስር መሰረቱ አጥንቶ፣ የመፍትሄ ሀሳብ እንዲያቀርብ፣ በቀድሞው የከተማ ልማትና ቤቶች ልማት ሚ/ር አቶ ሙኩሪያ ኃይሌ የሚመራ ከፍተኛ የመንግሥት ኃላፊዎች ያሉበት ዓቢይ ኮሚቴና ከየሚኒስትሩ መ/ቤቶች ኤክስፐርቶች ያሉበት የቴክኒክ ኮሚቴ ተቋቁሞ፣ ባለ 7 ነጥብ የጥናት ውጤት ለጠቅላይ ሚ/ሩ ቢያቀርብም፣ እስካሁን ድረስ አንዳችም መፍትሔ አልተሰጠንም ብሏል፤ የቤት ገዢዎች ኮሚቴ፡፡
ከቀረቡት 7 ነጥቦች መካከል፣ የአክሲዮን ማኅበሩን ህልውና በተመለከተ፣ ማኅበሩ በሕግ አግባብ የሚፈርስበት አግባብ እንዲፈለግና መብቶቹ ለቤት ገዢዎች እንዲተላለፍ፣ የኩባንያውን የመሬት ይዞታ በተመለከተ፣ ግንባታ ያልተካሄደባቸው ይዞታዎች፣ በአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር በኩል በፍጥነት በአደራ ወደ መሬት ባንክ እንዲገቡ፣ ግንባታ የተጀመረባቸው ይዞታዎች፣ ለግንባታ የወጣው ወጪ በመሃንዲሶች ተገምቶና የኮንትራክተሮች ወጪ ተቀንሶ ወደፊት ለቤት ገዢዎች እንዲዛወር፣ የኦዲት ሥራ ለቀጣይ እርምጃዎች ወሳኝ በመሆኑ በተቻለ መጠን በፍጥነት እንዲጠናቀቅ የሚል ይገኝበታል ያለው ኮሚቴው፤ ኩባንያው፣ ከቤት ገዢዎች በሰበሰበው ገንዘብ የተገዙ ከ30 በላይ የመሬት ይዞታዎች በአደራ ወደ መሬት ባንክ መግባታቸውን፣ ነገር ግን ባዶ መሬቶቹ ከሊዝ አዋጅና ሕግ ውጪ፣ በሕገ ወጥ መንገድ በግለሰቦች ኢ-ፍትሐዊ አካሄድ፣ ከ160 በላይ ቤቶች ገዢዎች ይሰሩበታል የተባለ ቦታ፣ በማያውቁት መንገድ ተሸጦ ማስመለሱንና እንደገናም መሸጡን አመልክተዋል፡፡
በፋይናንስ ኦዲት ሪፖት መሰረት፣ ከተሰበሰበው 1.4 ቢሊዮን ብር ውስጥ ለመሬት ንብረት ግዢ ከ271 ሚ. ብር በላይ፣ ለሥራ ተቋራጮ ከ178 ሚ. ብር በላይ፣ የተለያየ የጥቅም ግንኙነት ላላቸው የተከፈለ ከ245 ሚ. ብር በላይ፣ አቶ ኤርሚያስ አመልጋ ከኩባንያው የወሰዱት ከ59 ሚ. ብር በላይ፣ በተለያዩ ጊዜያት ለግለሰቦች የተከፈለ ከ66 ሚ. ብር በላይ፣ ለግንባታ ሥራ የዋለ ከ211 ሚ. ብር በላይ፣ ለኮሚሽን የተከፈለ ከ39 ሚ. ብር በላይ፣ ለልዩ ልዩ ወጪዎች ከ125 ሚ. ብር በላይ… ወጪ መደረጉን፣ ከ10 ሚሊዮን ብር በላይ ደግሞ ምንም አርዕስት የሌለው ሲሆን የተጠቀሱት ወጪዎች ከተሰበሰበው ገንዘብ በላይ ሲቀነሱ፣ በአጠቃላይ ከ900 ሚ. በላይ መባከኑ ተጠቁሟል። ኩባንያው ለሁለት ዓመት ከ2002-2004 የቦርድ አባላት እንዳልነበሩት፣ አቶ ኤርሚያስ ብቻቸውን እንደሚወስኑ፣ ብቻቸውን ትዕዛዝ እንደሚሰጡ፣ ፋይናንሱንም ብቻቸውን እንደሚያንቀሳቅሱ፣ በውሸት በፈጠሯቸውና አሁን በሌሉ ድርጅቶች ስም ከ59 ሚ. በላይ ወደ ኪሳቸው ከትተው የሚጠይቃቸው አካል ስለሌለ፣ በነፃነት በከተማዋ ይንቀሳቀሳሉ ብሏል፤ ኮሚቴው፡፡
ኮሚቴው ለጠቅላይ ሚ/ር ዶ/ር ዐቢይ አህመድ ባቀረበው ጥያቄ፤ ዜጎች በሀገራቸው የፍትህ ስርአት የሚተማመኑ፣ በነፃነት ሀብት የሚያፈሩባት የጋራ አገር እንድትሆን፣ በአክሰስ ሪል እስቴት ቤት ገዢዎች ላይ የደረሰው በደል፤ በሌሎች ሪል እስቴቶች እንዳይደርስ፣ እንዲያደርጉ፣ ይህ ዓይን ያወጣ ዝርፊያ በእኛ እንዲበቃ፣ አገርም ከሌቦች ፀድታ እንድትለማ ፅኑ እምነት አለንና፣ መንግሥት በገባልን ቃል መሰረት፣ የመጨረሻ ውሳኔ እንዲሰጠን፣ በጀመሩት የለውጥ እንቅስቃሴም ለጉዳያችን በአጭር ጊዜ ውስጥ ቁርጠኛ ውሳኔና አመራር እንዲሰጡልን እንጠይቃለን በማለት ተማፅኗል፡፡   

 ከዕለታት አንድ ቀን አንድ በኑሮው የደላው፤ ሀብቱ የተመቸው፣ እጅግ ቀብራራ ሰው፣ ነበረ፡፡ የሰፈር ሰው ሁሉ ደግና ለተቸገረ ደራሽ ነው ይለዋል፡፡ ወደ ቤተ - ዕምነት ሄዶ ሰባኪው የሚሉትን ይሰማል፡፡
ሰባኪው - በሀልዮ በነቢር በገቢር የተሰራ ሐጢያትን እግዚሐር ይፍታን
ምዕመናን - አሜን!
ሰባኪው - ለተቸገረ እርዱ!
      - በሽተኛ ጠይቁ!
      - ለደሀ መጽውቱ!
      - ሁለት ያለው አንዱን አንድ ለሌለው ይስጥ!
      - የላይኛው ቤታችሁን እምድር ሳላችሁ አብጁ!
      - ፁሙ! ፀልዩ!
      - ትምህርታችሁን ይግለጥላችሁ!
ምዕመናን - አሜን!
ሰባኪ - ከእናንተ የተሻለ የሚኖር ማን አለ?
ምዕመናን - ማንም!
ሰባኪ - ከእናንተ መካከል ሳይበላ የሚያድር ማን አለ?
ምዕመናን - ማንም!
ሰባኪ - ትሰጡት አትጡ!
ምዕመናን - አሜን!
ሰባኪ - በየመንገዱ የወደቁትን ለማሰብ ልቦና ይስጣችሁ!
ምዕመናን - አሜን!
ሰባኪ - የሰማነውን በየልቦናችን ያሳድርብን!
ምዕመናን - አሜን! አሜን!
ሁሉም ወደ የቤታቸው ሄዱ፡፡ ያም ሀብታም ሰው ወደ ቤቱ ለመሄድ መንገድ ጀመረ፡፡
ወደ ቤቱ መሄጃው ላይ አንድ ድልድይ አለ፡፡ እድልድዩ ላይ በግራና በቀኝ በኩል ተቀምጠው የሚለምኑ ሁለት ዓይነ - ሥውር ለማኞች አሉ፡፡ መካከላቸው ሲደርስ ከኪሱ በርካታ ሳንቲሞች አወጣ!
ለማኞቹ - “ጌታዬ አትለፈን! ካለህ አይጉደልብህ! ትሰጠው አትጣ! ትመፀውተው አትጣ! እጅህ እርጥብ ይሁን!” ይሉታል፡፡
ሀብታሙ ሰው ከኪሱ ያወጣቸውን ሳንቲሞች በሁለት እጆቹ ይዞ አንኳኳቸው፡፡ ሿ! ሿ! ሿ! አደረጋቸው፡፡ ሁለቱ ዐይነ - ስውር ለማኞች በጣም ጎመጁ፡፡ ከአሁን አሁን መጥቶ ይሰጠናል ብለው ሲጠብቁ, ሳንቲሞቹን መልሶ ኪሱ ከቶ፤
“ተካፈሉ!” ብሎ ሄደ፡፡
በወዲህ ወገን ያለው ለማኝ; “ያኛው ተቀብሏል፤ ያካፍለኛል” አለ፡፡
በወዲያ በኩል ያለውም ለማኝ፤
“እሱ ተቀብሏል፣ ያካፍለኛል!” አለ፡፡
ሁለቱም ምንም ሲያጡ ተነስተው አንዱ; “ስጠኝ! የሰጠንን አካፍለኝ!` ሌላውም; “ላንተ ነው የሰጠህ አካፍለኝ!”
`አንተ ወስደሃል … አንተ ወስደሃል” እየተባባሉ፤ ድብድብ ጀመሩ፡፡
ሀብታሙ ሰው; ከሩቅ ሆኖ ከት ብሎ ሳቀባቸውና ወደ ቤቱ ሄደ!
***
እኛ ኢትዮጵያውያን ደግ፣ እንግዳ ተቀባይ፣ ለተቸገረ ደራሽ፣ ተዛዛኝ … እንባላለን፣ እንጂ ጭካኔያችን ለከት የለውም! ውስጣችን አልተፈተሸም፡፡ አልተመረመረም! በሰብአዊነት ሽፋን የምንኖር ኢ-ሰብአዊዎች ነን! ፈዋሽ ሀኪም አልተገኘልንም እንጂ የውስጥ ደዌ አለብን - ጭካኔ! እንዋደዳለን እንላለን እንጂ ውስጣችን በጭካኔ አባዜ የተሞላ ነው! የመሀይምነታችንና የአረመኔነታችን (Barbarism) መጠን ገና አልታወቀም - አልተጠናንም! እርግጥ ሁላችንም ላንሆን እንችላለን እንጂ የክፋታችን ልክ ይህ ወሰንህ፣ ይህ ዲካህ የሚባል አይደለም፡፡ አያምጣው እንጂ ክፉ ጊዜ ቢመጣ፣ እርስ በርስ ሊያበላላን ይችላል! ነፃነት ይከብደናል! መከራ ከመልመዳችን የተነሳ ነፃነት ሸክም ይሆንብናል፡፡ ድህነታችን የሀብት ብቻ ሳይሆን የአዕምሮም ነው! የልቡናም ነው! ደግ ጊዜ ያምጣልን እያልን፣ ደጉን ጊዜ ገፍተን እንጥላለን! ይሄ ኃይለኛ የልቡና ቀውስ ነው! አዎንታዊ ነገር የማይጥመን ከሆነ፣ አሉታዊው ነገር በደም ጎርፍ ያስተጣጥበናል!
ሎሬት ፀጋዬ ገ/መድህን በቴያትሩ እንዳስቀመጠው፤
“ሞትን ለሚሻ ሞትን ነው መንፈግ! ህይወትንም አለመቸር! እማህል ቤት ነው የሰው ልጅ ጥቅም የሚሰጥ! ሰው ሆኖ ካሹት፣ ጥቅም የማይሰጥ የለም!” ይለናል፡፡ ለዚህ ፀሐፊ፣ የአበሻ ውስጠ ነገር ዱሮ ነው የገባው ማለት ነው!
ያም ሆኖ “በርኩቻው ማህል ፀጥ ብለህ ለመጓዝ ሞክር” ይላል፤ የጥንቱ የጠዋቱ የዴዚዴራታ ምክር! ምክሩ ከገባን ዓለም በውካታ የተሞላች ናት - አንተ ግን ተረጋግተህ ተጓዝባት ማለት ነው፡፡ መረጋጋት፣ ማረጋጋት፣ ሁኔታዎችን በሰከነ ዐይን ማየት፤ የበሳል ሰው መርህ ነው፡፡ “በካፊያው ከተረበሽክ የዶፉ ዝናብ ጊዜ ምን ይውጥሃል?” ይላሉ አበው፡፡ ህዝባችንን ማሳወቅና ማስተማር፣ መሰረታዊ ጉዳያችን መሆን አለበት፡፡ በክፋት፣ በጭካኔና በአረመኔያዊነት (Barbarism) እና በህዝባዊ እምቢተኝነት (Civil disabidience) መካከል፤ የገደል ያህል ልዩነት አለ፡፡ የፊተኛው የኃላ ቀርነት፣ የኋለኛው የአዋቂነት አስተሳሰቦች ናቸው፡፡ በመሰይጠንና በመሰልጠን መካከል ያለውን አደጋ እናስተውል፡፡ የዱሮ ፍልስፍናም ቢሆን “ህግ የማይገዛውን ነፃነት፣ ኃይል ይገዛዋል” የሚለውን አባባልም እንደገና ማውጠንጠን ግዴታ ሊሆን እንደሚችል አንዘንጋ፡፡ “ጥንቃቄ ሲጠብቅ ፍርሃት ይሆናል” የሚለውንም አንርሳ፡፡ ዞሮ ዞሮ የሚመለከተውና ኋላፊነቱ የሚሰማው ክፍል የሚያደርገውን ያውቃል ብለን እንገምታለን - “እኔ ተጎድቼ ባመጣሁበት ውሰደው” ይላል ጮሌ ነጋዴ፡፡
ሀገራችን ሾተላይ ያለባት ይመስል ፅንስ ይጨነግፍባታል፡፡ ማስወረድ ልማድ ሆኖባታል፡፡ አሮጊው እንቅፋት አዲስ እንቅፋት እየፈለፈለ ያሽመደምዳታል፡፡ “እኔ ስወለድ ነው የሳቅ ጀምበር የጠለቀችው” የሚል ኢትዮጵያዊ እንዳይበዛ፤ ልባም ልባሞቹ ሰዎች መመካከር አለባቸው፡፡ “ገዢ እንጂ መሪ አያምርብንም” እንዳለው አፍሪካዊው ፀሐፊ፤ በግድ የገዢ ያለህ እያልን እንዳንፀልይ ምህረቱን ይላክልን፡፡ ውድቀትን ማቀድ አልፎ አልፎ ያዋጣል ብንልም፣ መነሻችን ጨለምተኝነት ከሆነ፣ ከ“ሁሉም ይውደም ፍልስፍና” (nhilism) አባዜ አይተናነስም! “እኔ ከሞትኩ ሰርዶ አይብቀል” እንዳለችው እንስሳም፤ የአገር ጨለማን መባጀት ክፉ እርግማን ነው! የየዓይነቱን እርግማን በበቂ አይተናልና አዲስ እርግማን ፍለጋ መባቸር ከንቱ መላላጥ ነው፡፡ “ከመርገምት ሁሉ የከፋው መርገምት፤ ቋንቋ ለቋንቋ መጠፋፋት ነው!” ይላል ገጣሚው፡፡ መግባባት እንዳይጠፋብን አሳቢዎቻችንን (Thinkers) እናዳምጥ እንሰማማ!! እርስ በርስ እንናበብ፡፡ መናበባችንን ይባርክልን ዘንድ ቀና እንሁን፡፡ አገራችን ኢትዮጵያ ከእንግዲህ “ትወልዳለች እንጂ አታሳድግም” መባሏ መቆም አለበት፡፡ የበቀሉ ዕድሎች እንዳይጠወልጉ እንንከባከባቸው! እውቀታችንንና አቅማችንን ሁሉ አፍንጫችን ሥር ባለው ጉዳይ ላይ ሳይሆን ትልቁን ስዕል አገርን (The Bigger Picture) ማየት ላይ እናውለው፡፡ የግለሰቦችን ምንነት ከአጠቃላዩ ህዝብ ህልውና ለይተን እንይ! ዛሬም ትምህርታችንን ይግለጥልን!!