Administrator

Administrator

ጥንት ከዕለታት አንድ ቀን አንድ ዐረብ ፍርድ ቤት ይቀርባል፡፡ የከሰሱት ሶስት ሴቶች ናቸው፡፡ ያለአግባብ ፈቶናል፣ በድሎናል፣ ብለው ነው አቤቱታ ያቀረቡት፡፡
ዐረቡ ቀርቦ እያንዳንዳቸውን፤ “ለምን እንዳባረርካቸው አስረዳ?” ተባለ፡፡
ዐረቡም፤
“የመጀመሪያዋ ሚስቴ ጠዋት ማታ ጭቅጭቅ አበዛችብኝ!” አለ፡፡
“ምን ብላ ጨቀጨቀችህ?” አሉ ዳኛው፡፡
“ነገ ትፈታኛለህ፤ አላምንህም ትላለች፡፡ ሲሰለቸኝ እንደውም ‹ዛሬ ነው የምፈታሽ› ብዬ አስወጣኋት!”
“መልካም፡፡ ሁለተኛዋንስ?”
“ሁለተኛዋ ደግሞ የትላንትናዋን ሚስትህን እንዴት ፈታሃት? እያለች ነጋ - ጠባ ትነተርከኛለች፡፡ ‹አንቺ ስለትላንት ምን አገባሽ? የዛሬን በሰላም ኑሪ› ብላት አሻፈረኝ አለች፤ አባረርኳት!”
“ሶስተኛዋስ?”
“እሷ ደግሞ ‹ለነገ አታስብም› ትለኛለች፡፡ ‹የዛሬን መደሰት ብቻ ነው ፍላጎትህ፡፡ ነገም እኮ መኖር አለብን› ትላለች፡፡ ‹ዝም ብለሽ የዛሬን ተደሰች› ብላት እምቢ አለች - አባረርኳት!”
ዳኛው የሚስቶቹንም ቃል ከሰሙ በኋላ፣ “ፍርድ ቤቱ ሁኔታውን ካየና ግራ ቀኙን አመሳክሮ ከመረመረ በኋላና በተለይም ለማንኛዋም ባለቤትህ ምንም ንብረት አለማካፈልህን በማመንህ፣ አሁን ለሁሉም ካሳ ክፈል ብትባል ስለሚከብድህ፤ ሶስቱንም አግብተሃቸው እንድትኖር ተወስኗል!”
ዐረቡም፤
“ክቡር ፍርድ ቤቱ ትላንትን፣ ዛሬና ነገን አግብተህ ኑር ነው የሚለኝ?”
“አዎን፡፡ ውሳኔው እንደዚያ ነው፡፡”
“ባይስማሙልኝስ?”
“እሱን ስንደርስ እናየዋለን!”
“ነገም አላችሁ ማለት ነው?”
“ፍርድ ቤቱን አትዳፈር! የታዘዝከውን ፈፅም” አሉ ዳኛው በቁጣ፡፡
*   *   *
ፍትህና የፍትህ አካላት ነገር ሁሌም እንዳሳሰበን አለ፡፡ የተከማቹ ፋይሎች ጉዳይ፣ የቀጠሮዎች መራዘም ልማድ፤ እንደጤናማ ሂደት መቆጠር ከጀመረ ዘመናት አልፈዋል፡፡ “የፍርድ ቤት ሙግት አለብኝ” ይሉ የነበሩት አያት ቅድመ - አያቶቻችን ህይወት ዛሬ ይታያል ማለት ጊዜና ሁኔታን ያላገናዘበ ትዝብት ሆኖ ይሰማናል - anachronistic እንዲሉ፡፡ ያም ሆኖ ወደ ትላንት ተመልሰን እየኖርን ነው ባንልም፣ የትላንት ድባብ ስር እንድንጠለል የሆንን ይመስላል፡፡ የጥንት ፍርድ ቤቶች ዋና ሥራ የመሬት ሙግት እንደነበር ይታወቃል፡፡ ዳኞች ‹በጓሮ በር ሙክት ያስጎትታሉ›፤ ጉቦና እጅ መንሻ ምስሳቸው ነው ይባላል፡፡
“ተወኝ ዳኛ አዳኜ፣ የበግ መግዣም የለኝ እጅ እጄን የሚያዩ ብዙ ልጆች አሉኝ” ተብሎ የተገጠመው ቢቸግር ነው፡፡ ዛሬ ስሙ ሙስና የተባለው ጉቦ፤ የቤት ስሙ “ቢዝነስ”፣ “ኮሚሽን”፣ “የሥራ ማንቀሳቀሻ - ጉዳይ ማስፈፀሚያ” መሆኑ አይገርምም፡፡ “ጠበቃ ማንን ያዝክ?” እገሌን። “በጣም ጥሩ ሰው ይዘሃል፡፡ እሱ ዳኞቹን አሳምሮ ያውቃል!” ሙስና ፈርጁ ብዙ ነው፡፡ የፖሊስ ጣቢያ እስረኛ ስልኩ ተወስዶበት፤ በፖሊሱ ሞባይል ወደዘመዶቹ ለመደወል ብዙ ብር የሚከፈልበት አገር ፍትሕ እንዴት እንደሚገኝ ግራ ይገባል፡፡ ይህ ማለት ግን ሀቀኛና ጠንካራ አካላት የሉም ማለት አይደለም -ይዋጣሉ ነው ችግሩ! የሚገርመው በየመስሪያ ቤቱ ሲዘርፍ የከረመው ሁሉ አንደኛ የፍትህ ተቆርቋሪ ሆኖ መገኘቱ ነው፡፡ ዙሪያ - ገባው፣ ከልሂቅ እስከ ደቂቅ “ሌባ! ሌባ!” እያለ እየጮኸ ሳር - ቅጠሉን የሚግጥ ነው! ከቤተ - ሰባዊ የኮንትሮባንድ ንግድ ጀምሮ እስከ ኩባንያዊ ሽቀላ ድረስ አገሩን ያምሳል፡፡ ዛሬ ለበላይ አካል የሚያስፈልገው ጥያቄ የት ቦታ ሙስና አለ? ሳይሆን፤ የት ቦታ ሙስና የለም? የሚለው ነው፡፡ የመፍትሄው ቁልፍ ጥያቄ፤ የበላይ አካልን እገሌ ከእገሌ ሳይሉ መፈተሽ ነው፡፡ ሀቀኛ ጥናት ማካሄድ ነው። በሽርክና የተገባባቸው ንግዶችን፣ የኮንስትራክሽን እንቅስቃሴዎችን፣ በልማት ስም የሚሰሩ ደባዎችን ደፍሮ ማጣራትና ማጥራት ነው! አንድ ፀሐፊ እንደጠየቀው፤ “ይሄ የበላይ አካል ማለት የብዕር ስም ነው እንዴ?” ተብሎ መጠየቅ አለበት፡፡ የበላይ አካል ምስጢር መሆን የለበትም፡፡ በተማሪው ለመተማመን፣ አስተማሪውን መመርመር ነው፡፡ የፍትህ የበላይ አካላት፣ የኢኮኖሚ የበላይ አካላት፣ የፖለቲካ የበላይ አካላት፣ የትምህርት የበላይ አካላት … ሁሉም የበላይ ጠባቂ አላቸው፡፡ ሥረ - ነገራችን እንግሊዞች እንደሚያቀርቡት ጥያቄ “Who guards the guards?” ዓይነት ነው፡፡ “ጠባቂዎቹን ማን ይጠብቃቸዋል?” እንበልና ላዕላይ ጠባቂውንም በጥበብ እንመርምር፡፡

ሁሴን አዳል መሐመድ (ዶ/ር)

    ብሔር ወይስ ብሔረሰብ?
የቀበሌ፤ ወረዳ፤ ዞን ወዘተ ሕዝብ፤ ሕዝብ ነው፤
የብሔረሰብ ሕዝብ፤ ሕዝብ ነው፡፡
የብሔር ሕዝብ፤ ሕዝብ ነው፤
የኢትዮጵያ ሕዝብ፤ ሕዝብ ነው፡፡
ሕዝብ = አገር
አገር = ሕዝብ
ብሔር/ብሔረሰብ ሕዝቦች እያሉ በደፈናው ማነብነብና መጻፍ በአገራችን የተለመደ ነገር ሆኗል፡፡ የማህበረሰባዊ ጽንሰ ሓሳብ መግለጫዎች የሆኑት ሁለቱ ቃላት፤የአገራችን ፖለቲካ ንድፈ-ሓሳብ ማጠንጠኛ እንዲሆኑ በመደረጉ የማንም ባለ ወቅት ፖለቲከኛ ሰው፤ የፖለቲካ አፍ መፍቻ ይሁኑ እንጂ ከአገራችን ሕዝብ ተጨባጭ ሁኔታ አንጻር በእነዚህ ሁለት ቃላት መኻል ያለው አንድነትና ልዩነት በትክክል የሚታወቅ አይመስልም፡፡ ይህ ሆኖ እያለ ግልጽ ካልሆነ ጽንሰ-ሓሳብ ላይ ተነስቶ ቃላቱን የሕገ መንግሥት አንቀጽ አድርጎ እስከ መሄድ የተደረሰው በድፍረት መሆኑ በእጅጉ ያስገርማል፡፡
ብሔር/ብሔረሰብ፤ የማርክሲስት/ሌኒኒስት የማህበረሰብ ዕድገት ታሪክ፣ ቁስ አካልነት፣ ፍልስፍና ጽንሰ-ሐሳብ ሲሆን አንዱ ወይም ሌላው የሚገለጸው ከህብረተሰብ ታሪክ ወቅት ጋር ባለው ተዛምዶ፣ በአንድ የተወሰነ የታሪክ ወቅት የሚኖር ማህበረሰብ በማለት እንጂ በግል ስሜት አይደለም፡፡ ብሔረሰብን በዝቅተኛ የኢኮኖሚ ደረጃ ማለትም በፊውዳላዊ ወይም ቅድመ ካፒታሊዝም የኢኮኖሚ ደረጃ ውስጥ የሚገኝ ማህበረሰብ እንደሆነ ሲገልጹ፤ ብሔር ደግሞ ከፊውዳሊዝም መክሰም በኋላ ከካፒታሊዝም ማደግ ጋር ተያይዞ የተዋሃደና በከፍተኛ የዕድገት ደረጃ ላይ ያለ፣ የጋራ ኢኮኖሚ ሕይወት ያለው ማህበረሰብ እንደሆነ ይገልጻሉ፡፡ ከዚህ ጽንሰ-ሐሳብ አኳያ አሁን በአንድ ክፍለ ዘመን እየኖሩ ካሉት የኢትዮጵያ ብሔረሰቦች ሕዝቦች የትኛው፣ በየትኛው የታሪክ ወቅት እየኖረ ነው? ኢትዮጵያ አሁን በስንት የታሪክ ወቅት ውስጥ ትገኛለች? ብሔሩ የየትኛው አስተዳደር ክልል ሕዝብ ነው? ብሔረሰቡስ? ደቡብ፤ ኦሮሞ፤ አማራ፤ ትግራይ፤ ሱማሌ፤ አፋር፤… ብሔር ወይም ብሔረሰብ ለመሆን አሟልተው የተገኙት መስፈርት ምንድን ነው? የትኛው በፊውዳሊዝም ስልተ-ምርት ይገኛል? ወደ ካፒታሊስት ስልተ-ምርት እየገሰገሰ ያለ ወይም የሚያደርገውን ሽግግር ያጠናቀቀው የትኛው ነው? እያንዳንዱ መልስ የሚያሻው ጥያቄ ነው፡፡ ስለ ፌደራሊዝምና ዲሞክራሲያዊ ብሔረተኝነት የሚኖረን ዕውቀት፣ ከማነብነብ እልፍ እንዲል ከፈለግን፣በሁለቱ ላይ የጠራ ግንዛቤ መያዝ ያስፈልገናል፡፡
በቀዳማዊ ኃይለ ሥላሴ ዩኒቨርሲቲ (ቀ.ኃ.ሥ.ዩ) ታጋይ ተማሪዎች የተራገበው፣ በአገራችን ተጨባጭ ሁኔታ ላይ ያልተመሰረተው የማርክሲስት/ሌኒኒስት፣ የብሔር/ብሔረሰብ ጽንሰ-ሓሳብ፣ የሜዳ ትግል ስልት የመረጡትን ወጣቶች፣ በአገራችን ታሪካዊ ጠላቶችና ባልነቃ ብሶተኛ ሕዝብ ድጋፍ፣ ለሁለት አስርተ ዓመታት ጫካ ውስጥ አክርሞ፤ በጦር ሜዳ ያልተሰውቱን ታጋዮች፣ ለቤተ መንግሥት ከማብቃቱ በስተቀር በጽንሰ-ሓሳቡ ላይ የጠራ ግንዛቤ ባለመያዙ፣ ለችግሩ መቋጫ የሚሆን መፍትሔ እስከ አሁን አልተገኘም፡፡ አገራችን ሌላ ዙር ትርምስ የሚጠብቃት ይመስላል፡፡ በደርግ ላይ ድል መቀዳጀት፣ አጼ ምኒልክ ቤተመንግሥት ካስገባ በኋላ፣ ቀ.ኃ.ሥ.ዩ ተጠንስሶ፣ ጫካ ውስጥ ተደፍድፎ፣ የፈላውን ያልጠራ ጽንሰ-ሓሳብ የመንግሥት/ገዥ ፓርቲ የፖለቲካ ሰነድ በማድረግ፣ ማንኛውንም ሓሳብ ሳያቅማሙ የሚቀበሉ ዜጎችን ከየብሔረሰቡ ተወላጆች አስጠግቶ በመጋት፣ በእነርሱ መንኩራኩርነት ለማስፋፋት የተደረገው የትግል እንቅስቃሴ፤ ሕዝባችንን ለእንግልት፤ አገራችንን ለውርደት አጋልጧል፡፡
በቅጡ ካልተረዱት ጽንሰ-ሓሳብ በመነሳት የጠባብ ብሔረተኝነት ትግል አስፈላጊነትን በእንጭጭ አእምሯቸው በመቀበል፣ ለአገራችን ታሪካዊ ጠላቶችና የገዥ መደብ ዝንባሌ ለነበራቸው ቡድኖች ፍላጎት ማሳኪያ በረሐ ገብተው፣ የተደናበረው ትግል ትሩፋት ተቋዳሽ ሆነው ከቆዩ በኋላ፣ ዘግይተውም ቢሆን ሁኔታዎችን በሰከነ አእምሮ ማገናዘብ የቻሉ፣ ራሳቸውን ወደ ዳር ያገለሉ፣ አንዳንድ የቀድሞ ወጣቶች/የአሁኖቹ አዛውንቶች፣ ላሳለፉት የዜሮ ድምር የበረሐ ትግል ፍጻሜ፣ በየተራ እየተጸጸቱ ንስሐ በሚገቡበት በአሁኑ ጊዜ፣ “ጉድ ሳይሰማ አይታደርም” እንዲሉ፣ የአገራችንን የመከራ ዘመን ለማራዘም መጥበብ በማይችል ብሔረሰብ ስም ጭምር የጠባብ ብሔረተኝነት ትግል ጥንስስ የሚጠነስሱ፣ የማህበረሰብ ክፍሎች ብቅ ብቅ ማለታቸው አስደንጋጭ ነው፡፡
እዮሃ! እዮሃ!
የጎመኑ ዘመን ውጣ፤ የጮማው ግባ እንዲሉ፤
የብሔረሰብ ፓርቲ ዘመን ይሻር፤
የርዕዮተ ዓለም ፓርቲ ዘመን ይንገሥ፡፡
--እንደ ማለት፣ የጠባብ ብሔረተኝነት ገመድ በመጓተት፣ አገራችን ከአንዱ የዘመን አሮንቃ ወጥታ በሌላ የዘመን አሮንቃ! ውስጥ እንድትርመጠመጥ ይተጋሉ፡፡ በወዳጅና ጠላትነት ሁልጊዜ በደም ስንፈላለግ እንድንኖር ይሻሉ፡፡ ቀጥሎ የቷን “ብሔር”፣ “ህብረተሰባዊ ዕረፍት ለማሳጣት” ነው፡፡ እሺ ቀጥሎስ? ወደ ቀድሞ ገናናነታችን የሚመልሱን ሠረገላዎች፣ የብሔረሰብ ፓርቲዎች ይሆኑ እንዴ? በርካታ ብሔረሰቦች ሕዝቦች በሚኖሩባት ውድ አገራችን፣ የሚፈጠር የፖለቲካ አስተሳሰብ ቅኝት፣ ሁሉንም የአገሪቱን ዜጎች ሊያሳትፍ ከሚችል የጋራ ርዕዮተ ዓለም አውድ ይልቅ በብሔረሰቦች ልዩነቶች ላይ እንዲመሰረት የሚደረግበት ምክንያት ምንድን ነው? እርግጥ ነው፤ የፖለቲካ አስተሳሰብ ቅኝትን በርዕዮተ ዓለም አውድ ላይ እንዲያተኩር ማድረግ የፖለቲከኛን የአስተሳሰብ ከፍታና በሰፊ የፖለቲካ ስነ ምህዳር ውስጥ በነጻ መወዳደርን ይጠይቃል፡፡ ይህ አቅም በሌለበት፤ ዘወትር በኪራይ ሰብሳቢነት ለመኖር በጠባብ ብሔረተኝነት የፖለቲካ አንቀልባ መታዘል፣ አዋጭ የፖለቲካ አማራጭ ይሆናል፡፡   
ኤሎሄ ኤሎሄ፤
ለማ ሰበቅታኒ፡፡
ከእንግዲህ ወዲያ የብሔረሰብ ፓርቲ ስህተት፣ ያለፈ ታሪካችን አካል ሆኖ መቅረት እንጂ መቀጠል የለበትም። ምንም እንኳ ለጠባቦች የኪራይ መሰብሰቢያ፣ጊዜያዊ የንግድ ፈቃድ ወረቀት ሆኖ ቢያገለግልም ያለፈው ስህተት ያስከተለው ዕዳ፣ የብሔረሰቡ ሕዝብ ዕዳ ብቻ ከመሆን አልፎ ለሌሎች ብሔረሰብ ሕዝቦች በአጠቃላይ ለመላው የኢትዮጵያ ሕዝብ የተረፈ የጋራ ዕዳ ነው፡፡ እርግጥ የአማራ ብሔረሰብ ሕዝብ በይበልጥ ስለመጎዳቱ አስረጂዎች በግልጽ እየቀረቡ ይገኛል፡፡
የብሔረሰብ ፓርቲ፤ ዘመን ተሻጋሪ፣ መልካም ውርስ አይደለም፡፡ ጠባቦችን ላለፈው ስህተታቸው ንስሐ ለማስገባት ግፊት ማድረግ እንጂ ፈለጉን በመከተል አዳዲስ የብሔረሰቦች ፓርቲዎችን መፍጠር ለምንወዳት አገራችን፤ ኢትዮጵያ አንድነት መቀጠል አይረባንም፡፡ አገራችን ተነጣጥለው የቆሙ ብሔረሰቦች ሕዝቦች የሏትም፡፡ ለምሳሌ በአማራ ሕዝብ ስም ጠባብ የብሔረሰብ ፓርቲ አቋቁሜ እታገላለሁ የሚል ቡድን ቢነሳ፣ ሁኔታው ከማስደንገጥ አልፎ ያስፈራል፡፡ ይህ የማይቀር የሚሆነው ሌሎች ከጠባብነት ሐዲድ መውጣት ተስኗቸው፣ ያንኑ የጠባብነት ገመድ ነክሰው ባሉበት እየረገጡ ከቀጠሉ ብቻ እና ብቻ መሆን ይኖርበታል፡፡ ያኔ! ለአማራ ሕዝብ መጥበብ የሕልውና ጥያቄ ስለሚሆንበት የጠባብ ቡድን ዓላማን መሸከም የግድ ይላል፡፡ በኢትዮጵያዊነቱ የሚኮራ፤ ለኢትዮጵያ አንድነት ዘብ የሚቆም ትምክተኛ ሕዝብ በመባል በጠባብ ቡድን ኃይሎች ሲጠራ የኖረ ታላቅ ሕዝብ፤ እሱነቱን እንደ ባዶ ስልቻ አቅልሎ ወደ እዚህ ዝቅተኛ ደረጃ መድረስ ግድ ከሆነበት የጠባብነት ትግሉን ፈር ለማስያዝ፣ በመጀመሪያ የአማራ ሕዝብን አገር ወሰን ዳርቻ ማስመር፤ ብሎም ከዳር ድንበሩ ውጭ ስለሚኖረው የአማራ ሕዝብ ዕጣ ፈንታ ሁነኛ አቅጣጫ ማስቀመጥ ግድ ይለዋል፡፡
“የእኛ ቡድን ብሔር መሬት ያን ሁሉ ያጠቃልላል”፤ “ጨቋኟ የአማራ ብሔር፣ ህብረተሰባዊ ዕረፍት አታገኝም” እያለ ሲወተውት የነበረ ጠባብ ቡድን፤ በምስጢር የነደፈው የአስተዳደር ክልሎች አወቃቀር ለአገራችን እንደ ማይበጅ አንዳንድ ነባር የቡድኑ አባላት በጸጸት ስሜት ምስክርነት እየሰጡ ነው፡፡ የኤርትራ ከእናት አገሯ መገንጠል፤ አገራችን የባህር በር ማጣት፣ ኢሕአዴግ የፈጸመው ታሪክ ይቅር የማይለው ጥፋት/ንዝህላልነት መሆኑን ሳያወላውሉ በማውገዝ፣ ላለፈ ክረምት ቤት ከሚሠሩ ነባር ታጋዮች ጎን ለጎን፣ ልቦና የማይገዙ ደቀ-መዝሙሮች መኖራቸው ያስገርማል፡፡
ፌደራሊዝምና ዴሞክራሲያዊ ብሔረተኝነት፤ “የአገራችን ሕልውናና የአብሮነት መሰረቶች” ናቸው የሚለውን ጥርት ያለ ሐቅ የሚክድ ዜጋ ያለ ይመስል፣. ዘወትር ንግግር በማሳመር፣ እምቧ ከረዩ የሚሉ አንዳንድ የመንግሥት/የገዥ ፓርቲው ባለስልጣናት አሉ፡፡ ችግሩ ፍትሐዊ በሆነ መንገድ አለመተግበሩ ስለመሆኑ መናገር ድክመት መስሎ ይታያቸዋል፡፡ ዴሞክራሲያዊ ብሔረተኝነት ያለ መከባበርና መዋደድ አይመጣም፡፡ በፌዴራሊዝምና ዴሞክራሲያዊ ብሔረተኝነት ዙሪያ በአገራችን የነበረው ያለፈ ዘመን መልካም ገጽታ፤ በአሁኑ የአስከፊ ዘመን መስታወት ውስጥ በግልጽ እየታየ ለመሆኑ ከዚህ በላይ ማስረጃ የለም፡፡ እስካሁን ድረስ በአገራችን የሰፈነውን የአተገባበር ጉድለት መንስዔ፤ ዓላማና ግብ እንደዚሁም ፋይዳ የሚያውቁት ምስጢረኞቹ ብቻ ነበሩ፡፡ ከቅርብ ጊዜ ወዲህ ግን የምስጢሩ እሽግ ፖስታ ተከፍቶ በመነበቡ ምክንያት ምስጢሩ ለአብዛኛው ዜጎች ግልጽ ሊሆን በመቻሉ፣ ሕዝቡ በዕውቀት ላይ ለተመሰረተ ትግል ተነሳስቷል፡፡
ባለፉት 27 ዓመታት አገራችን ክፉኛ አዘቅት ውስጥ የወደቀችበት ችግር መንስኤው የፌደራሊዝም ቅርጸ-መንግሥት መዘርጋቱ ሳይሆን የፌደራሊዝም ስርዓቱን ያዋቀርንበት መርህ-አልባ የአወቃቀር ንድፍ ነው፡፡ ጥቂት መገለጫዎችን እስቲ እንይ፡
አንዳንዴ ቋንቋን ወሳኝ መስፈርት በማድረግ ማህበረሰቦች የምንነት ጥያቄ ይዘው እንዲቀርቡ በማድረግ ለቀረበ የምንነት ጥያቄ አስቸኳይ ምላሽ ይሰጣል፤ አዲስ የአስተዳደር ክልል ወዲያውኑ ይፈጠራል ወይም ማህበረሰቦች ወደ አንዱ ክልል ይካተታሉ፤
ቋንቋውን ባይችልም ተካትቶ ሲያበቃ፣ ቋንቋ እንዲማር የሚወሰንበትም አለ፤
ቋንቋው ጭራሽ በመጥፋቱ የተነሳ በሚናገሩት ቋንቋ ብቻ ከሌላው ምንነታቸውን መለየት የሚያስቸግሩትን የማህበረሰብ ክፍሎች፤ በመንግሥት ድጋፍ፤ የምንነት መጠሪያ ስም አውጥተው ከነባር የማህበረሰብ ዘውግ እንዲለያዩ ይደረጋል፤  
የምንነት ጥያቄ ማቅረብ የሚያስጠይቅበት እና የምንነት ጥያቄ እንዲቀርብ ግፊት የሚደረግበት ክልል ጎን ለጎን አለ፡፡
“ከልጅ ልጅ ቢለዩ በሞት ይለዩ” የሚሉ ማህበረሰቦች ደግሞ ጆሮ ዳባ ልበስ ይባላሉ፡፡
በማይመስለን ክልል ተቀርቅረናልና፣ መልሱን፣ የሚሉ ማህበረሰቦች ደግሞ መከራ ይከፍላሉ። ማህበረሰቦቹ ይመስለናል የሚሉት ክልላዊ አስተዳደር፤ አንዴ አሳልፎ ለሌላው ስለሰጣቸው ፊት ይነሳቸዋል፤ የወሰዳቸው ክልል ደግሞ መብታቸውን በመጠየቅ፣ ክፉኛ አሳጡኝ በሚል “ካፈርኩ አይመልሰኝ” ድርቅና ነገሮችን ሁሉ ያጠብቅባቸዋል፡፡ መብትን መጠየቅም ስለሚያስጠይቅ ማህበረሰቦቹ በ”እከክልኝ፣ ልከክልህ”ተደጋግፎት ይሰቃያሉ፡፡
ማህበረሰቦቹ በሰሚ ዕጦት፣ ከሁለት የወጣ ጎመን ሆነው በመንከራተት፣ከመጠውለግ ወደ መድረቅ ተጠግተዋል፡፡ የወልቃይት፤ የራያ ሕዝቦች ችግር ይኸው ነው፡፡
ብሔረሰባዊ ምንነት ተፈጥሯዊ የሆነና ማንኛውም ሰው ከተገኘበት ብሔረሰብ ጋር አብሮ የሚወለድ ወይም በማህበራዊ መስተጋብር በሚፈጠር አጋጣሚ ወይም በምርጫ የሌላውን ብሔረሰብ ምንነት በመያዝ ሊገኝ እንደሚችል ተቀባይነት ያገኘ መርህ ነው፡፡ ከዚህ መርህ አንጻር የአንድ ብሔረሰብ ቋንቋ ተናጋሪ መሆን ብቻውን ለብሔረሰባዊ ምንነት አያበቃም፡፡ ቋንቋ ብቻውን ብሔረሰባዊና አገራዊ ምንነትን ገላጭ ዋና መስፈርት ተደርጎ ሊወሰድ አይችልም፡፡ በሚናገሩት ቋንቋ ብቻ ማህበረሰቦችን፣ የዚህ ብሔረሰብ አባላት ናቸው ማለት ቋንቋ የሚጋሩ የሁለት ጎረቤት አገሮች ማህበረሰቦችን፣ የአንድ አገር ዜጎች ናቸው ማለት ያለመቻል ያህል ነው፡፡
ለሚቀርቡ የምንነት ጥያቄዎች በርካታ መስፈርቶችን ተጠቅሞ፤ ከሁሉም በላይ ደግሞ የማህበረሰቡን ታሪካዊ ዳራ አጥንቶ፤ በማህበረሰቡ ፍላጎት ላይ ተመስርቶ፤ በጥንቃቄ ተመልክቶ፣ በወቅቱ መልስ የማይሰጥ ከሆነ፣ እንዲሁም አድሏዊ አሰራር ካለ፤ የቃልና የተግባር አንድነት እጥረት አጋጥሟል፤ ተቀባይነት አግኝቷል የሚባለው መርህ ተጥሷል ማለት ነው፡፡ ለምንነት ጥያቄ መልስ በሚጠብቅ ማህበረሰብና ጉዳዩ በሚመለከተው ውሳኔ ሰጭ አካል መኻል፣ የጥቅም ግጭት የወለደው ቅራኔ ይታያል፡፡ እቅጩን ለመናገር ደጋግሞ መነገር ያለበት ጉዳይ በአገራችን የደረሰው ህብረተሰባዊ ችግር መንስዔው ለድብቅ የቡድን ፍላጎት ማሳኪያ ሲባል፣ በፌደራሊዝም ስም፣ ሕዝቡን በቋንቋ ግድግድ አጥር አካልሎ በማናቆር የተፈጠረው የመልካም አስተዳደር ችግር ነው፡፡ ሕዝቡ የሚያነሳቸው ኢ-ፍትሐዊ የሐብት ክፍፍል፤ ሙስናና ሌሎች ጥያቄዎች፣ በተዋረድ የሚገኙ የዋናው ችግር መገለጫዎች ናቸው፡፡
በብዝህነት ላይ ሲያተኩር ለሕዝቦች አንድነት ዝቅተኛ ትኩረት የሰጠው በብሔረሰብ ምንነት መስፈርት ላይ የተመሰረተው አዲሱ የአስተዳደር ክልሎች አወቃቀር፣ ወደ ፊት የሚያስከትለውን ችግር ባለማጤን ማህበረሰቦችን ያለ ይሁንታቸው ለዘመናት አብሮ በመኖር በጋራ ከመሰረቱት የማህበረሰብ ዘውግ በማፈናቀል ለያይቷቸዋል፡፡ የአካባቢ አስተዳደር አወቃቀሩ በአካላዮቹ ራዕይ መሰረት፤ በቋንቋ ልዩነት ላይ የተገነባ በመሆኑ ዜጎችን በአገራቸው የሚኖሩ ባይተዋሮች አድርጓቸዋል፡፡ ይህ ሆኖ እያለ አዲሱ የአስተዳደር ክልሎች አወቃቀር ተበታትነው የቆዩ የብሔረሰብ ሕዝቦችን አንድ ላይ በማሰባሰብ በብሔረሰቦች ሕዝቦች መካከል ጠንካራ ግንኙነት ለመፍጠር ያስቻለን ህብረተሰባዊ ዕድገት ነው በማለት ይቀለዳል! “ዓሳን ከባሕር አውጥቶ ማንሳፈፍ፣ ለጭልፊት ርሕራሄ ይመስላታል” እንዲሉ አበው! ዳሩ ግን ምንም ያህል ጠቃሚ ይሁንም አይሁንም፤ አዲሱ የአካባቢ አስተደደር ክልል አወቃቀር የተከናወነው ከሕዝብ ውሳኔ ውጭ ነበር፡፡ የባለራዕዮችን ውሳኔ ዝም ብሎ እንዲቀበል ነው የተደረገው፡፡ ሕዝቡ ከክልል ስያሜ አሰጣጥ ጀምሮ አልመከረበትም፡፡ ክልሎች በመነሻው ላይ በቁጥር ተሰየሙ፤ ቀጥሎ ስም ሲወጣ እያንዳንዱ ስም እንዴት እንደወጣ ሕዝቡ አያውቅም። በመጨረሻም ያስከተለው ውጤት ታየ፡፡ አብዛኛው ዜጋ የስነልቦና ጉዳቱን ተሸክሞ፣ ከዚህ የተሻለ ቀን በተስፋ እየጠበቀ ነው፡፡   (ይቀጥላል)


    በህክምና ባለሙያው ቸርነት ገብረ ክርስቶስ የተፃፈው በህክምና ላይ የሚያጠነጥን “ዲባቶ” የተሰኘ መፅሐፍ ለንባብ በቃ፡፡
መፅሐፉ በዋናነት በህክምናው አለም ያሉ የአካሚና የታካሚ እውነቶችን በስነ ፅሑፍ ለዛ እያዋዛ እውቀትና ግንዛቤ የሚያስጨብጥ ነው ተብሏል፡፡ በ371 ገፆች የተቀነበበው መፅሐፉ በ160 ብር እና በ20 ዶላር ለገበያ ቀርቧል፡፡  

 በኢትዮጵያ ለመጀመሪያ ጊዜ በአገር አቀፍ ደረጃ የመገናኛ ብዙኃን ሽልማት ሊካሄድ መሆኑን የሽልማት አዘጋጁ ዋይጂኤስ መልቲ ሚዲያ አስታወቀ፡፡ የሽልማት ሥነ ሥርዓቱ በብሮድካስት ባለስልጣን እውቅና እንዳገኘ የገለፁት የድርጅቱ ኃላፊዎች፤  የሽልማት ሥነ ሥርዓቱ ነሐሴ 26 ቀን 2010 ዓ.ም በብሔራዊ ቴአትር አዳራሽ እንደሚካሄድ ጠቁመዋል፡፡
በዕለቱም በህትመት፣ በብሮድካስትና በድረ ገፅ መገናኛ ብዙኃን ከፍተኛ አስተዋፅኦ ያደረጉና የተመረጡ ጋዜጠኞች እንደሚሸለሙ ተገልጿል፡፡ ተሸላሚዎች የሚመረጡት በዘርፉ የካበተ ልምድና ብቃት ባላቸው የመገናኛ ብዙኃን ባለሙያዎች ዳኝነት እንደሆነም ለማወቅ ተችሏል፡፡ የሽልማቱ አዘጋጅ ዋይጂኤስ መልቲ ሚዲያ ከአሁን በፊት የተለያዩ የኪነ ጥበብ መድረኮችን በማዘጋጀት የሚታወቅ ሲሆን በአሁኑ ወቅት በብስራት ኤፍ ኤም ሬዲዮ ላይ “ማራኪ” የተሰኘ ፕሮግራም የሚያቀርብ ድርጅትም ነው፡፡

የእውቁ ፖለቲከኛና መሐንዲስ ኢ/ር ዘለቀ ረዲ፣ “የ21ኛው ክ/ዘመን መሳፍንትና ኢትዮጵያን እንደ ሀገር የማስቀጠል ፈተና” የተሰኘው መፅሐፍ የፊታችን ሰኞ ከቀኑ 11፡00 ጀምሮ በዋቢ ሸበሌ ሆቴል ይመረቃል፡፡
በምርቃት ስነ ስርዓቱ ላይ የመፅሐፉ  ዳሰሳ (review)፣ እንዲሁም ከመፅሐፉ የተመረጡ ክፍሎች የሚቀርቡ ሲሆን ውይይትም ይደረጋል ተብሏል፡፡

• የብሔር ፖለቲካ ባለበት፣ ሊበራል አስተሳሰብ በድንገት ቢመጣ ጥሩ አይሆንም
  • ከኤርትራ ጋር መደራደር ስለተፈለገ ብቻ መደራደር ይቻላል ወይ?
  • የጠ/ሚኒስትሩ የጎረቤት አገራት ጉብኝት አንደምታው ብዙ ነው

    ታዋቂው የፖለቲካ ሣይንስ ምሁር ፕ/ር መድህኔ ታደሰ በዶ/ር አብይ ሰሞንኛ እንቅስቃሴዎች ፣ በኤርትራ እና ኢትዮጵያ ግንኙነት፣ በቀይ ባህር ጉዳይ... ከአዲስ አድማስ ጋዜጠኛ አለማየሁ አንበሴ ጋር ተከታዩን ቆይታ አድርገዋል፡፡
      ፕ/ር መድህኔ ታደሰ (የፖለቲካ ተንታኝ)


    የጠ/ሚኒስትሩን የሥራ እንቅስቃሴ እንዴት አገኙት? በተለይ በክልሎች እየተዘዋወሩ፣ ከህዝብ ጋር የሚያደርጓቸው ንግግሮችና ውይይቶች? ----
የጠቅላይ ሚኒስትሩ እንቅስቃሴ በአጠቃላይ ከፖለቲካዊ ማዕቀፍ አንፃር ነው መታየት ያለበት። የእሳቸው ቅቡልነት ከኢህአዴግ ውጪ ባሉትም ያመዘነበት፣ የህዝብን ስሜት የያዙበት ሁኔታ ነው ያለው፡፡ በየአካባቢውና በየክልሉ ከተለያዩ የህብረተሰብ ክፍሎች ጋር መወያየታቸው፣ ቅቡልነታቸውንና ተፈላጊነታቸውን የሚያሳድጉበት አንድ መንገድ ነው። በሌላ በኩል ከነበረው የጨለምተኝነትና የስጋት ስሜት፣ ህዝቡንና ሀገሪቱን ተስፋ ወደሚፈነጥቅበት ምዕራፍ ለማሸጋገር የተጠቀሙበት አካሄድ ነው ተብሎ ሊወሰድ ይችላል፡፡ መንግስት ከአሁን በኋላ ህዝቡን እያዳመጠ፣ የተለያዩ ፖለቲካዊ ማሻሻያዎች፣ የፖሊሲ ማሻሻያዎች ወዘተ-- ማድረግ አለበት፡፡ ለዚህ ደግሞ ከህዝቡ ጋር እንዲህ ባለው መንገድ ቀጥታ ተገኝቶ መወያየት ጠቃሚ ነው፡፡ ከህዝቡ የሚያገኙት ግብአት፣ ፖሊሲያቸውን ለመቀመር ያስችላቸዋል፡፡
ጠቅላይ ሚኒስትሩ በድርጅታቸው የተሟላ ድጋፍ ባያገኙም በመጪው ነሐሴ ጉባኤ ማካሄዱ አይቀርም። እስከዚያው ድረስ ከህዝቡ ጋር ተነጋግረው፣ የድርጅታቸውን የወደፊት አቅጣጫና ትክክለኛ ማንነት በሚያስረግጥ መልኩ ስራዎች ለመስራት ከተፈለገ፣ እንደዚህ አይነት እንቅስቃሴዎች ማድረግ ተገቢ ነው። ጠቅላይ ሚኒስትሩ ብዙ ነገር እያደረጉ ነው፡፡ አሁን ባለው ተጨባጭ ሁኔታ ከዚህ በላይ  ማድረግ የሚችሉ አይመስለኝም፡፡
ጠ/ሚኒስትሩና የሚመሩት ድርጅታቸው ኢህአዴግ ምንና ምን ናቸው ?
ግንባሩ በድርጅት የማንነት ቀውስ ውስጥ ነው ያለው፡፡ የእሳቸው ወደ ስልጣን አመጣጥ አንደኛው ምክንያት፣ የፖለቲካ ውጤት ብቻ ሳይሆን አንድ የተቀየረ ነገር እንዳለ አመላካች ነው፡፡ ኢህአዴግ ድሮ የሚመራበትና ራሱን አጥሮ የሚያስርበት ዲሞክራሲያዊ ማዕከላዊነት፣ የተዳከመበት ደረጃ የደረሰ ይመስለኛል፡፡ እሳቸው የተለየ፣ ወደ ሊበራል የሚያደላ፣ ለዘብ ያለ የፖለቲካ መስመር የመያዝ አዝማሚያ ነው የሚታይባቸው፡፡ ሊበራል አመለካከት ሲባል እንግዲህ ኒዮሊበራል ነው ወይስ--? የሚለውን ማየት ያስፈልጋል፡፡ በሂደት መውጣቱ አይቀርም፡፡ በፓርቲው ውስጥ የሚደረገውን ውስጠ ትግል፣ከህዝብ ተፈላጊነትና ቅቡልነት አንፃር ለማካሄድ የፈለጉ ይመስለኛል፡፡  አጠቃላይ እንቅስቃሴያቸው፤ፖለቲካዊ ነው ማለት ይቻላል፡፡ እንቅስቃሴያቸው በኢህአዴግ ውስጥ ያለውን የኃይል ሚዛን ጭምር ታሳቢ ያደረገ ነው የሚመስለው፡፡ የመጡበት መንገድ ሲታይ፣ የሚሄዱበትም መንገድ፣ የፖለቲካ ውድድርና ፉክክር የሚታይበት ስለሆነ፣ ለዚያ ውድድርና ፉክክር፣ የተወሰነ እምቅ አቅም ለማግኘት ያሰቡ ይመስላል፡፡
ጠ/ሚኒስትሩ፤ የሀገሪቱን የፖለቲካ ችግሮች መፍታት ከፈለጉ፣ በቅድሚያ ከፖለቲካ ኃይሎች ጋር ድርድር ማድረግ አለባቸው የሚሉ ወገኖች አሉ፡፡ እርስዎ  ምን ይላሉ?
ምን ይዘው ነው በቅድሚያ ከፓርቲዎች ጋር ይደራደሩ የሚባለው? ለመደራደር ፍኖተ ቀመር ያስፈልጋቸዋል፡፡ እኚህ ሰው ወደ ስልጣኑ የመጡት በፓርቲው የውስጥ ዲሲፕሊንና አሰራር ተደግፈው አይደለም፡፡ በአለመስማማት መሃል ነው የመጡት። የተለያዩ የኃይል እና የስልጣን ማዕከላት፣ የተለያዩ የተቃዋሚ ኃይሎች---ባሉበት ሀገር፣ በመጀመሪያ ከተለያዩ የህብረተሰብ ክፍሎች ጋር ተነጋግረው፣ የህዝቡን ፍላጎት እንዲታይ አድርገው፣ ፓርቲያቸውን ማስተካከልና መለወጥ አለባቸው፡፡ ይሄን መልክ ሳያስይዙ፣ በምን መልክ? በምን ሰነድ? በምን ፍኖተ ካርታ? ነው ሊደራደሩ የሚችሉት? በሌላ በኩል ጠ/ሚኒስትሩ ይዘውት የመጡት አስተሳሰብ አለ። ሙሉ ለሙሉ ከኢህአዴግ ባይለይ እንኳ በተወሰነ አቅጣጫው ሊለይ ይችላል፡፡ ኢህአዴግ ውስጥ ባለው የሃሳብ የበላይነት ተፈትሾ ነው ተግባር ላይ የሚውለው። እሳቸው አዲስ አቅጣጫቸውን መሬት ባላወረዱበት ሁኔታ እንዴት አድርገው ነው ከተቃዋሚዎች ጋር የሚደራደሩት? ተቃዋሚዎችስ ምን ያህል ለድርድር ተዘጋጅተዋል? የሚለው አጠያያቂ ነው፡፡ ይሄ አሁን የሚያደርጉት እንቅስቃሴ፣ ሃሳባቸውን ለህዝቡም ለፓርቲያቸውም ይፋ እያደረጉ፣በሀሳባቸው ዙሪያ ኃይል የሚያሰባስቡበት ነው የሚሆነው፡፡  
ለወደፊት ስትራቴጂ ቀርፆ ለመደራደርና የፖሊሲ ለውጥ ለማምጣት ይሄ አካሄዳቸው ጠቃሚ ነው። ወደ ሊበራል አቅጣጫ ለመሄድም ብዙ ጥናት የሚጠይቅ ነገር አለ፡፡ ዝም ብለው ቸኩለው ከገቡበት ለራሳቸውም ለፓርቲያቸውም ለሃገርም አይበጅም። የብሔር ፖለቲካ ባለበት ሃገር፤ ሊበራል አስተሳሰብ በድንገት ቢመጣ ጥሩ አይሆንም፡፡ በሂደት ነው ነገሮች መታየት ያለባቸው፡፡ ለምሳሌ አንዳንዱ፣ ለምን የአስቸኳይ ጊዜ አዋጁ አልተነሳም ይላል፡፡ የአስቸኳይ ጊዜ አዋጁ ለፖለቲካ ውድድር በሚያመች መልኩ መቀመር አለበት፤ በተለይ የፀጥታና የደህንነት መዋቅሩ፡፡ እሳቸው የሚያመቻቸውን የአካባቢያዊና አጠቃላይ ሀገራዊ የደህንነት ሁኔታ መፍጠር አለባቸው፡፡ ይሄ ደሞ ጊዜ ይፈልጋል፡፡ የአስቸኳይ ጊዜ አዋጁ ይነሳ የሚለው ጥያቄ፤ አሁን ያለውን ሽኩቻና ችግር በጥልቀት ካለመረዳት የሚመነጭ ይመስለኛል፡፡
በጎረቤት አገራት ያደረጓቸው ጉብኝቶች---እንዴት ይገመገማሉ?
እነዚህ ጉብኝቶች በሶስት አቅጣጫ ነው መተንተን ያለባቸው፡፡ አንዱ የተለመደው የጉርብትና እና የዝምድና አቅጣጫ ነው፡፡ ይሄ ኢኮኖሚውንም፣ ፀጥታውም ይነካል፡፡ አላማውም እነዚህን ነገሮች ማጠናከር ነው፡፡ ሁለተኛው አካባቢያዊ አንድምታው ነው፡፡ አካባቢያዊ አንድምታው ሲባል የኤርትራ የደቡብ ሱዳን፣ የሶማሊያና የቀይ ባህር አካባቢ ሁኔታ ማለት ነው፡፡ ሶስተኛው የውስጥ የፖለቲካ አንደምታ ነው። ወደ ሱዳን ሲኬድ፣ ወደ ኬንያ ሲኬድ፣ ወደ ጅቡቲ ሲኬድ ብዙ የሚያገናኙን ነገሮች አሉ፡፡ ለምሳሌ፡- ወደ ጅቡቲ ሲኬድ፣ የአፋርና የኢሳ ጉዳይ አለ፡፡ በሶማሌና በኦሮሚያ ያለውን አንዳንድ ያልተገባ ሁኔታ ማንም የሚያውቀው ነው፡፡ ይሄ ከጅቡቲ ሱማሌዎች ጋር በምን ይገናኛል? የአፋር ጉዳይም አለ፡፡ ስለዚህ በሦስተኛ ደረጃ መታየት ያለበት፤ የኢትዮጵያን የፖለቲካ ሁኔታ፣ በውስጥ በራሳቸው ስልጣን የማጠናከር ጉዳይ ነው፡፡ ይሄን ካላደረጉ የአካባቢ ህልው አደጋ ላይ ይወድቃል ማለት ነው፡፡ ለምሳሌ አቶ መለስ ከመሞታቸው በፊት በፃፉት ደብዳቤ፤ “ከኦብነግ ኃይል ጋር አስታርቁን” ብለው ኬንያን ጠይቀው ነበር፡፡ እዚያ ኬንያ ውስጥ በኦጋዴን ጉዳይ ከፍተኛ ተሰሚነት ያላቸው ሰዎች አሉ። እሱ ላይም ለመነጋገር ጉብኝታቸው አስፈላጊ ሊሆን ይችላል፡፡ እነዚህ ነገሮች ስላሉት ለየት ሊል ይችላል። በኤርትራ በኩል ደግሞ የመታረቁ ነገር ከአሜሪካኖቹ ግፊት የመጣ ሊሆን ይችላል፡፡ ከኤርትራ ጋር ለመታረቅ ኢትዮጵያ ብቻዋን ዘው ብላ መግባት አለባት? ወይስ ከወዳጆቿ ጅቡቲና ሱዳን ጋር ማቀናበር አለባት? ይሄ አንዱ ወሳኝ ሁኔታ ነው፡፡
በሌላ በኩል፤ የግድቡ ጉዳይ አለ፡፡ ይሄም ታሳቢ መደረግ አለበት፡፡ ለምሳሌ ሱዳንና ኢትዮጵያ፤ ከፍተኛ የሆነ ወታደራዊ ስምምነት አላቸው፡፡ ይሄን ጉዳይ ተነጋግረው፣ የሃገሪቱን ሉአላዊነት ከማስከበር አንፃር መልክ ማስያዝ አለባቸው፡፡ ሌላው የደቡብ ሱዳን ጉዳይ ነው፡፡ ከሱዳንና ከኬንያ ጋር አንድ አቋም መያዝ ሊያስፈልጋቸው ይችላል፤ለዚህም መነጋገር አለባቸው። ጉብኝታቸው አካባቢያዊ፣ ሁለትዮሻዊ እና የውስጥ ፖለቲካ አንድምታ አለው፡፡
ሃገሮች የተጠናከረ ኢኮኖሚያዊ ትስስር ካላቸው፣ በፀጥታና በፖለቲካ ጉዳይ ለከባድ ችግር አይጋለጡም። ከዚህ አንፃር በተለየ ሁኔታ በኢኮኖሚ መተሳሰር ያስፈልጋል፡፡ ለምሳሌ ወደብ የኤሌክትሪክ ኃይል አቅርቦት፣ የውሃ አቅርቦት፣ የባቡር መስመር ዝርጋታ የመሳሰሉ ይገኙበታል፡፡  እነዚህ በሀገራቱ መካከል የጋራ ጥቅም ላይ የተመሰረተ ኢኮኖሚያዊ ትስስር ለመፍጠር አጋዥ ናቸው፡፡ የጋራ ጥቅም ካለ ፖለቲካው አይጎዳም። እርስ በእርስ መጠባበቁ ይኖራል፡፡
በውጭ የሚያደርጉት ጉዞ ከዚህ አንፃር ሲታይ፣ በውስጥ ያለውን ሰላምና መረጋጋት ለማምጣት የሚደረገው ጥረት አካል ሆኖ ነው መታየት ያለበት። ለመጀመሪያ ጊዜ በህዝብ ጫና ጠቅላይ ሚኒስትር የሆነ የኦሮሞ ተወላጅ፣ በኬንያ ኦሮሞዎች ላይ ተፅዕኖ የለውም ማለት ይከብዳል፡፡  ከዚህ አንፃር ከኦነግ ጋር ወደ ሰላም ድርድር ሊገባ ይችል ይሆናል፡፡ ስለዚህ የውጭ ሃገሩ ጉብኝታቸው አንድምታው ብዙ ነው፡፡
በኤርትራ እና በኢትዮጵያ መንግስታት መካከል ሰላም መፍጠር ይቻላል ብለው ያስባሉ?
ፍላጎቱ በኢትዮጵያውያንም፣ በኤርትራውያንም፣ በውጭ መንግስታትም አለ፤ በአካባቢው መንግስታትም እንዲሁ፡፡ አሁን የሚያስፈልገው ሁለቱ ሀገራት የሚደራደሩበትን መነሻ ሐሳብ ማዘገጀትና ማጠናቀር ብቻ ነው፡፡ ምክንያቱም የኤርትራ መንግስት አቋም ልክ ጦርነቱ እንደተጀመረበት ወቅት ነው ያለው። የሁለቱ ሃገራት ሁኔታ ያኔ በጦርነቱ ጊዜ እንደነበረው ነው፡፡  
የፀቡ መነሻ የሆነ መሬት ለኤርትራ ተወሰነ፤ የኤርትራ መንግስት ደግሞ ያንን መሬት ለድርድር እንደ ቅድመ ሁኔታ፣ይዞት ቀጠለ፡፡ የኤርትራ መንግስት አንገብጋቢ የሆነበት የባድመ መሬት ቢሰጠው እንኳ በበጎ አይን ይደራደራል ተብሎ አይጠበቅም። ምክንያቱም መነሻው ባድመ አይደለም፡፡ ሁለተኛ የሰላም ዋስትና ባድመ አይደለም፡፡ የኤርትራ መንግስት ባህሪ፤ ለኢትዮጵያ በጎ አመለካከት ያለው መሆኑን በምን ልናረጋግጥ እንችላለን? ይሄን ማረጋገጫ ማንም ሊሰጥ አይችልም፡፡ ኤርትራን ወደ ሰላም እናምጣ የሚሉ የአሜሪካ ፖለቲከኞችም ይሄን ሊያረጋግጡ አልቻሉም፡፡ ስለዚህ ከኤርትራ ጋር ድርድር ማድረጉ ለምን ውጤት ነው?
የኤርትራ ፖለቲካል - ኢኮኖሚ መርህ እስካልተቀየረ ድረስ የሰላም ሂደቱ በቀላሉ የሚከናወንና የሚፈፀም አይደለም፡፡ ከኤርትራ ጋር መደራደር ስለተፈለገ ብቻ መደራደር ይቻላል ወይ? ይሄም ሌላው ጥያቄ ነው፡፡ ሌላው በአካባቢው የቻይና መምጣት፣ ከየመን ሁኔታ ጋር፣ ከአሜሪካ የቀይ ባህር የጦር ኃይል ጋር፣ ቀይ ባህር ደግሞ ለኤርትራም ሆነ ለኛ ስትራቴጂካዊ ቦታ ነው ከሚል መነሻ ነው ውጤት መምጣት ያለበት። የሚፈለገው ምንድን ነው? የሁለቱ ሀገራት ሰላም መሆን ነው? ወይስ ቀይ ባህር ላይ ያላቸውን ጥቅም ከማስከበር አኳያ ነው? የሚለው ግልፅ አልወጣም። ይሄ ግልፅ ባልወጣበት ሁኔታ፣ የመሬት ልውውጥ ጉዳይ ብቻ ከሆነ ዋጋ የለውም። የሰላም ሂደቱ መጀመር ያለበት ቀጠናውን ባገናዘበ መልኩ ነው፡፡ ባድመ የሰላማዊ ግንኙነቱ መነሻ ነው መሆን ያለበት፡፡ አሁን ግን ባድመን ለብቻዋ ነጥሎ የመውሰድ ሁኔታ ነው፣ በኤርትራ በኩል ያለው፡፡ ያ ከሆነ ምንም ውጤት የለውም፡፡
ዶ/ር አብይ፤ የቀንዱ አካባቢ ጎረቤት ሃገራትን መጎብኘታቸው፣ የኢትዮጵያን ተፅዕኖና ሚና በማስጠበቅ ረገድ  ከዶ/ር አብይ በቀጠናው ጉዳይ ምን ይጠበቃል?
ቀጠናው ላይ የኢትዮጵያ ሚናን ለማጠናከር ወሳኙ የውስጥ ሰላምን ማጠናከር ነው፡፡ በመጀመሪያ እሳቸው የሀገሪቱን የውስጥ ሰላም ማጠናከር አለባቸው፡፡ የውስጡን ሁኔታ እንዳይጎዳም የጎረቤት ሃገራትን ግንኙነት ማጠናከሩም ጠቃሚ ነው፡፡ አሁን እንደሚያደርጉት ማለት ነው፡፡ በወሳኝ መልኩ ኢትዮጵያ በአካባቢው የሰላም እና የማረጋጋት ሚናዋን ልታጠናክር የምትችለው ግን የኢትዮጵያ የፖለቲካ ሂደት ሰላማዊ፣ ዲሞክራሲያዊ እና በንግግር ላይ የተመሰረተ ሲቪላዊ የፖለቲካ ሂደት ሲፈጠር ነው፡፡ የውስጧ ሰላም የተረጋገጠ ሃገር፤ የአካባቢው የኃይል ሚዛን ወደሷ ያደላል፡፡ አሁን የህዝብ ቁጥር የበላይነት አላት፤ ወታደራዊ የበላይነት አላት፣ ጥንታዊ የመንግስት አወቃቀርና ስርአት ያላት ሃገር ነች፣ ኢኮኖሚዋ እያደገ የመጣ ሃገር ነች፤ መሃል ላይ ነው ያለችው፡፡ ከዚህ አንፃር መሬት ላይ ያላት ኃይል ጠቃሚ ነው፡፡ ነገር ግን ይሄን ኃይሏን ተጠቅማ በቀይ ባህር አካባቢ ያላትን ሚናዋን እንዳትወጣ፣ አስሮ የያዛት የውስጥ የፖለቲካ ቀውስ ነው፡፡
 ዶ/ር አብይ፤ ይሄን የውስጥ ቀውስ በመፍታት፣ ሰላማዊ የስልጣን ሽግግር በማምጣት፣ ዲሞክራሲያዊ ተቋሞች በማጠናከር --- የሃገር ውስጥ የፖለቲካ ሂደቱን ማስተካከል ለኢትዮጵያ አካባቢያዊ የበላይነት ወሳኝ መሆኑን የተረዱ ይመስላል፡፡ ከዚህ አንፃር እዚህ ላይ ማተኮራቸው አይቀርም፡፡ እስከዚው ድረስ የውጪ ኃይሎች የሚያበላሹት ነገር ይኖራል፡፡ ለምሳሌ የዩናይትድ አረብ ኤምሬትስ እና የእነ ኳታር በሶማሊያ ጉዳይ የሚያደርጉት ነገር አለ፡፡ ይሄን ከኬንያ፣ ከኢጋድ ጋርም ተነጋግሮ ወደ አፍሪካ ህብረት በአጀንዳነት ማምጣት ያስፈልጋል፡፡ የቀይ ባህር ጉይ ለቀንዱ ሃገራት በሙሉ የደህንነት ጉዳይ ነው፡፡ የወደብ እና የኮንቴነር ጉዳይ አይደለም ቀይ ባህር የደህንነት ቀጠና ነው፡፡ ለኢትዮጵያ ቀይ ባህር የደህንነት ቀጣና ነው። ይሄ የደህንነት ጉዳይ ኢጋድን የአፍሪካ ህብረትን ይመለከታል፡፡ ስለዚህ ከእነዚህ ሃገሮች ጋር መነጋገር ይሄን አጀንዳ ወደ ላይ ከፍ የማድረግ ሙከራዎች ዶ/ር አብይ እያደረጉ ያለ ነው የሚመስለኝ በጉብኝታቸው። ማድረግ ያለባቸውም ይሄንኑ ነው፡፡ ዋናው ግን የኢትዮጵያን የውስጥ የፖለቲካ ሃዲድ ማስተካል ለኢትዮጵያ ቀጠናዊ የበላይነት ወሳኝ ነው፡፡ ተፅዕኖ ፈጣሪነቱም የሚመጣው ከዚህ በመነጨ ነው፡፡  

ለመሆኑ ስንቶች ይሆኑ በትዳር አለመታመን የተነሳ ወደ አልሆነ አቅጣጫ እየተጉዋዙ በስነተ ዋልዶ ጤና ችግር የታወኩ? ይህንን ጥያቄ ለመመለስ እራሱን የቻለ ጥናት ቢያስፈ ልገውም በየአቅራቢያችን ግን የታዘብናቸው ብዙ ክስተቶች አሉ፡፡ በቤታቸው ውስጥ ሆነው ልጆቻቸውን ከማሳ ደግ እና ባልን ከመርዳት ውጭ ደጁን የማያውቁ በኤችአይቪ ምክንያት ለህልፈት የተ ዳረጉ ብዙዎች ናቸው። ቤተሰባቸውን ለማስተዳደር ሲሉ ጧት ማታ ከመማሰን እና ከሚስቶቻ ቸው ውጭ ሌላ ሴት የማያውቁ ብዙ ወንዶች በግብረስጋ ግንኙነት ምክንያት በሚተላለፉ በሽታ ዎች ኤችአይቪን ጨምሮ የተጠቁ ብዙዎች ናቸው።  ምናልባትም ልቅ የግብረስጋ ግንኙ ነት መፈጸም ከአመል ወይንም ከባህርይ ጋር ብቻ የሚያያዝ አለመሆኑን እና ይልቁንም በትዳር መካከል ከሚኖር አለመግባባት ወይንም ታማኝነት ማጣት በመሳሰሉት የሚከሰት መሆኑን ብዙ ጥናቶች ያስረዳሉ፡፡ መረጃ ዎች በትክክል ይህን ያህል ቁጥር ብለው ባይገልጹም በስፋት በአለም ላይ ሪፖርት የተደረገው ግን በዚህና በመሳሰሉት ምክንያቶች 60% የሚሆኑ ወንዶችና 40% የሚሆኑ ሴቶች በትዳር ዘመናቸው ከትዳር ውጭ ከሌላ ፍቅረኛ ጋር እንደሚገናኙ (Live-  about) የተሰኘ ድረገጽ ያስነ ብባል፡፡
Mort – Ertel የተባሉ የስነ ልቡና ባለሙያ ደግሞ ትዳር ለከፋ የጤንነት፤ የኢኮኖሚና ማህበራዊ ችግር ተጋልጦ ተጋቢዎችን ብቻ ሳይሆን ዙሪያውን ያሉ ቤተሰቦችን ከዚያም በላይ በህብረተ ሰብና በአገርም ላይ ችግር ከማስከተሉ በፊት ተጋቢዎች ሊያጤኑዋቸው የሚገባቸው ነገሮች አሉ ይላሉ፡፡  
የመጀመሪያው ችግርን ወደጎን መተው ነው፡፡
አንድን ትዳር ከመፍረስ ለማዳን ችግርን እንዴት መፍታት እንዳለባቸው ባለትዳሮች አስቀድ መው ሊያውቁ ይገባል። አንዳቸው ከአንዳቸው በምን አይነት መንገድ መግባባት ወይም መገናኘት እንዳለባቸው በስርአተ ጾታው ረገድም ያለውን ልዩነት ዘልቆ መመልከት ይገባል ይላሉ ባለሙያው። ይህንን ርእሰ ጉዳይ በሌላ ሙያ የተካኑ ባለሙያዎች ወይም ከሕክምና አንጻር በመመልከት ችግሩን ለመፍታት ቢሞከር እንኩዋን ትዳርን ማዳንና እንደነበረ ለመጠበቅ መፍትሔው የሚገኘው በራሳቸው በባለጉዳዮቹ እጅ መሆኑ ልብ ሊባል ይገባል ይላሉ የስነልቡና ባለሙያው። Mort – Ertel የቀረበላቸው የትዳር አጋሮች የህይወት ልምድ አላቸው፡፡ ታሪኩ እንደሚከተለው ነው፡፡  
‹‹….እኔና ሚስቴ ትዳራችንን የመሰረትነው አንዳችን ለአንዳችን በፍቅር ወድቀን ነው፡፡ ለፍቅራ ችን እጅግ ጥልቅ ስሜት ነበረን፡፡ በየምሽቱ ስናወራ፤ አንዳችን ለአንዳችን ያልተጠበቀ ወይንም አስደናቂ ስጦታዎችን ስንቀባበል ፤አንዳችን አንዳችንን ስናቀማጥል፤ ብቻ ባጠቃላይ አንዳችን ከአንዳችን ውጭ ምንም የምናስበው ነገር ሳይኖር በደስታ እየኖርን ነበር፡፡ እኛ በጣም የምና ስቀናና ለሌሎች ምሳሌ የምንሆን ፍቅረኞች እና ባለትዳሮች ነበርን፡፡   
ነበርን የሚለው ቃል አለምክንያት አልመጣም፡፡ የሁዋላ ሁዋላ ግን ይህንን እ…ፍ…ፍ..ያለ እንደእሳት የሚንቦገቦግ ፍቅር የሚያጠፋ ነገር ተከሰተ፡፡ ይህ ደግሞ የብዙዎችን ትዳር የሚፈ ትን መሆኑ ግልጽ ነው፡፡ አንድ ልጅ ተወልዶ ገና በሳምንት እድሜው ሞተ፡፡ ከዚያም መንትያ ሴት ልጆች ወልደን እነርሱም ገና በጨቅላነት እድሜያቸው አለፉ፡፡ ከዚህ በሁዋላ ሚስቴ በእ ኔም ባይሆን እንኩዋን በጠቅላላው በተፈጠረው ነገር በጣም እየተደበረች መጣች። ይህ ደግሞ በትክክል የሚጠበቅ ነገር ሲሆን እየዋለ እያደረ ግን በእኔና በእስዋ መካከል ችግር መፍጠሩ አልቀረም፡፡ እኔም እራሴን በስራ በጣም መጥመድ እና ጊዜ እንዳይኖረኝ መጣር ጀመርኩ፡፡ ሁለታችንም በየፊናችን መሮጥ እንጂ እንደድሮው መገናኘታችንን አፍ ለአፍ ገጥሞ ማውራታ ችንን እየተውነው መጣን፡፡ እንዲ ያውም ሳንተያይ ውለን ማታ አልጋ ላይ ብቻ አንዳችን አን ዳችንን መኖራችንን የምናረጋግጥበት አጋጣሚ በዛ፡፡ ሶስት ልጆቻችንን ካጣን በሁዋላ ሁሉም ነገር የተለየ ሆነ፡፡ ምሽቱን በሙሉ ሳቅ ጨዋታ ቀርቶ ኃላፊነትን በሚጠይቁ ጉዳዮች ጥቂት ንግግር ብቻ ተተካ፡፡ ማቆላመጥ ቀርቶ በሚያናድድ መልክ መጠራራት ጀመርን፡፡ ባጠቃላይም ግንኙነታችን ጸጥታ የመላበትና ብዙም የማያገናኘን እየሆነ መጣ፡፡
በእርግጥ ሁለታችንም ሁኔታዎች አስገድደውን እንጂ ይህ እንዲሆን አልፈለግንም፡፡ ስለዚህ ትዳ ራችንን ወደነበረበት ጤናማ ሕይወት ለመመለስ ሁለታችንም አንደምንፈልግ ተግባብተናል፡፡ ግን ወደፍቅር የሚወስደውን ጉዞ በሚመለከት አንዴ እኔ ስጀምረው እስዋ ትተወዋለች፡፡ እስዋ ስትጀምረው ደግሞ እኔ ችላ እላለሁ፡፡ በዚህ መልክ እንደቆየን አንድ እርምጃ ለመውሰድ ቁር ጠኝነቱን አሳየን፡፡  
መፍትሄው ምን ሆነ?
እማኞቹ እንደሚሉት በምን መንገድ ችግሮቻችንን መፍታት እንዳለብን የቻልነውን ያህል አነበብን፡፡ የግጭት ማስወገጃ ዘዴዎችን ጥቅም ላይ ለማዋል ጥረት አደረግን ይላሉ፡፡ ለምሳሌም፡-
...ውዴ…ምን ነበር ያልሽኝ…አልሰማሁሽም…እስቲ አድምጪኝ ልድገምልሽ…አንቺ ያልሽውን ተረድቼ እንደሆነ አድምጪኝ እና አረጋግጪልኝ፡፡
…የኔ ፍቅር …ተረድተኸኛል? ይሄ ነገር እኮ እንደዚህ ቢሆን ጥሩ ነበር፡፡ አይመስልህም?
…ጨመር አርገሽ ብዪ እንጂ…ትንሽ እኮ ነው የበላሽው…፤
…ይርድሀል…ይህን እስቲ ደርብበት…፤
የመሳሰሉትን የማግባቢያ እና አንዱ ለአንዱ የሚሰ ጠውን ክብርና መተሳሰብ የሚያሳዩ ድርጊቶችንና አባባሎችን ተጠቀምን፡፡ እንዲሁም ወደተለያዩ መዝናኛዎች በመሄድ ችግሮቹን ለመፍታት ሙከራ አደረግን፡፡ ነገር ግን ያነበብ ናቸው መጽ ሐፎች፤ የሄድንባቸው የምክር አገልግሎቶች ሁሉ የሚነግሩን ችግርን አለማንሳትን ሳይሆን እያነሱ መፍትሔ መፈለግ የሚል ስለሆነ ለእኛ ምንም ጥቅም አልሰጠንም። እንዲያውም ይበልጥ ያጣላን ጀመር፡፡ ድካማችን ምንም ለውጥ አላመ ጣም፡፡ የምንነጋገራቸውና የምናደርጋቸው ድርጊቶች የይምሰል ሆኑብን፡፡ ስለዚህም ሁለታችንም ከልባችን በግልጽ ለምን ለውጥ ማምጣት እንዳልተቻለ ተነጋገርን፡፡ በስተ መጨረሻም የራሳችንን ዘዴ ቀየስን፡፡ ጊዜ ወስደን ተወያየን፡፡ አንዳችን አንዳችንን አሳመንን፡፡ በቃ፡፡ እባካችሁ …ተጋቢዎች …ትዳራችሁ ችግር ገጥሞት ከሆነ …ይህንን ሞክሩ፡፡ ››ይላሉ የራሳቸውን ምስክርነት የሰጡት ባለትዳሮች፡፡
መፍትሔ ሆኖናል ያሉት የሚከተለውን ነበር፡፡ ‹‹ገጥሞን የነበረውን ችግር ምንነት ሁለታችንም ለየራሳችን በመረዳት ወደጎን አስቀመጥነው፡፡ በእነዚህ ችግሮች ዙሪያ በድጋሚ መነታረክም አልፈለግንም፡፡ ይልቁንም… ግንኙነታችን በተለየ ሁኔታ እንዲቀጥል ያለንን አቅም በሙሉ ተጠቀምን። አስቀድሞ የተፈጠረውን ችግር እያነሱ ከመታገል ወይንም አንቺ ነሽ …አንተ ነህ …እያሉ ከመነታረክ ምንም ይልቅ ምንም እንዳልተፈጠረ አድርጎ ለምን በአዲስ መልክ ኑሮአችንን አንቀጥልም ተባባልንና ተግባባን፡፡ ምክንያቱም በውስጣችን ያለውን ፍቅራ ችንን ሊያደበዝዝ የሚችል ምንም መሰረታዊ የሆነ ጉዳት አንዳችን በአንዳችን ላይ አልፈጸም ንም፡፡ ስለዚህ  አንዳንድ ለየት ያሉ መንገዶችን ተጠቀምን፡፡ ትዳራችን በአዲስ መልክ እንደገና እንዲቀጥል ለማድረግ አዳዲስ ልማዶችን ባህሪዎችን በማምጣት አንቺ ትብሽ አንተ ትብስ በመ ባባል በሚያስገርም ሁኔታ አንዳችን በአንዳችን እቅፍ ውስጥ እንደገና ወደቅን፡፡ ፍቅር እንደገና ብለን አዲሱን የትዳር ሕይወት መንገድ ተያያዝነው፡፡ ተፈጥሮ የነበረው ችግር ከእኛ ፍላጎት ውጭ እና ከአቅማችን በላይ በሆነ ምክንያት መሆኑን አምነን አንዳችን ለአንዳችን ቀና የሆነ አስተሳሰብ እንዲኖረን የቻልነውን ያህል ሞከርን። ተሳካልንም፡፡›› ብለዋል፡፡
የስነልቡና ባለሙያው Mort – Ertel የእነዚህን ተጋቢዎች ምስክርነት ይጋሩታል፡፡ ብታምኑም ባታምኑም ይላሉ ባለሙያው...ይህ ለብዙዎች ችግር ለገጠማቸው ትዳሮች እንደ በጎ ምሳሌ የሚቆጠር ነው፡፡ ሁልጊዜም ማድረግ የሚሻለው ከተፈጠሩት ችግሮች እርቆ በተቃራኒው ግን በጎ የሆነ ግንኙነትን ለመፍጠር በተፈጠረው ወይንም ባሉበት ሁኔታ ላይ በግልጽ ተነጋግሮ አቅምን ለበጎ ነገር ማዋል ነው ፡፡ይህ ከሆነ ችግሮች ይሳሳሉ፤ ትዳር ከመፍረስ ይርፋል፤ የሌሎች በትዳር መሐል የሚከሰቱ ጣልቃ ገብነቶችም ይገታሉ ብለዋል የስነልቡና ባለሙያው፡፡   ይቀጥላል፡-

ዴሞስቴን የተባለ የግሪክ ፈላስፋ ህዝብ በተሰበሰበበት ንግግር ለማድረግ እየተሳነው ስለተቸገረ፤ የንግግር ልምምድ ለማድረግ ወደ አንድ ወንዝ አጠገብ ይሄዳል፡፡
ወንዙ በከፍተኛ ፍጥነት እየተወረወረ ቋጥኝ ላይ ያርፍና ኃያል ድምፅ ይፈጥራል፡፡ ዴሞስቴን ደግሞ ይህንን ድምፅ ለማሸነፍ እጅግ ነጎድጓዳማ ድምፅ ያወጣል፡፡
ወንዙ በቀጣይ ጩኸቱን ተያይዞታል፡፡ ፈላስፋውም የፉክክር ንግግሩን ያምባርቃል፡፡ ፈላስፋው ይህን ልምምዱን ለተወሰነ ወቅት ካካሄደ በኋላ ወደ ህዝብ መሰብሰቢያው አደባባይ ተመለሰ፡፡ ስብሰባው ተዘጋጀለት፡፡
ወደመናገሪያው መድረክ ወጥቶ፤
“የአቴና ህዝብ ሆይ!” አለና ቀጠለ፤ “ዛሬ ስለአቴና ችግር በሰፊው ልነገራችሁና ላስረዳችሁ ነው ፊታችሁ የቆምኩት!” አለ በጣም ጮክ ብሎ፡፡
ህዝቡ ጆሮ አልሰጥ አለው፡፡ እርስ በርሱ እያወካ፣ ጨርሶ መደማመጥ ጠፋ፡፡ ዴሞስቴን በተቻለው ድምፅ ጮሆ እየተናገረ ነው፡፡ ሰሚ ግን ጠፋ፡፡
በመጨረሻ፤ የሞት ሞቱን ጮሆ፡-
“የአቴና ህዝቦች ሆይ፤
የአንዲት አህያ ታሪክ ልነግራችሁ ነው፤ አሁን …”
ቀስ በቀስ የህዝቡ ጩኸት ቀነሰ፡፡ በመካያውም ፀጥ እርጭ አለ፡፡ ጀመረ ዴሞስቴ፡-
“ከዕለታት አንድ ቀን፣ አንዲት የምትከራይ አህያ የነበረችው አንድ ሰው ነበረ፡፡
በዚያው ወቅት አንድ ነጋዴ የሚከራይ አህያ ፍለጋ ወደ ባለአህያው መጥቶ፤
“ባለ አህያ?” ይለዋል፡፡
ባለ አህያ - “አቤት፤ ምን ልታዘዝ?”
ተከራይ - “የሚከራይ አህያ ፈልጌ ነበር?”
ባለ አህያ - “ውሰዳታ!”
ተከራይ - “ስንት ነው ሂሳብ?”
ባለ አህያ - “ለስንት ቀን?”
ተከራይ - “ለሶስት ቀን”
ባለ አህያው ዋጋውን ነግሮ, አህያዋን አስረከበውና ተከራይ ቀብድ ከፍሎ፣ አህያዋን ይዞ ሄደ፡፡
አንድ ቀን አልፎ ሁለተኛው ቀን ላይ ባለ አህያው ተከራይ በሄደበት መንገድ ወደ ገበያ ለመሄድ ጉዞ ጀመረ፡፡ ፀሐዩ በጣም ያቃጥላል፡፡ ምንም የጥላ መጠለያ የሌለበት፣ ጭው ያለ ሜዳ ነው፡፡ የአህያዋ ተከራይ አህያዋን አቁሞ፣ ጥላዋን ተጠልሎ ተቀምጧል፡፡
ባለአህያው ቀረብ ብሎ፤
“አስጠጋኝና አብሬህ ጥላው ስር ልቀመጥ” አለው
ተከራዩ - “አይቻልም”
ባለአህያ - “አህያዋኮ የራሴ ናት”
ተከራይ - “ትሁና! ዛሬን ጨምሮ እስከ ሦስት ቀን ድረስ የራሴ ናት”
ባለአህያ - “እንዲያውም፣ አህያዋን እንጂ ጥላዋን አልተከራየኸኝም - ለጥላዋ አስከፍልሃለሁ!”
ተከራይ - “ለሱ ሌላ ውል መፈራረም ይኖርብናል”
በዚህ ሁኔታ ሲጨቃጨቁ ቆዩ … አለና ዴሞስቴን ንግግሩን አቆመው፡፡
ህዝቡ፡-
እባክህ ጨርስልን! የዚህን መጨረሻ ሳናዳምጥ በጭራሽ ወደ ቤታችን አንሄድም!! እያለ አደባባዩን በጠበጠ!
“የአቴና ህዝብ ሆይ!
እጅግ አሳሳቢ የሆነውን የአቴና ችግር ላሳውቃችሁ ስናገር አልሰማ ብላችሁ፣ የአንድ አህያ ተረት መጨረሻ ለማወቅ ጓጉታችሁ ትጮሃላችሁ! ታሳዝናላችሁ! የአህያዋን ተረት መጨረሻ የምነግራችሁ፣ የአገራችሁን አቴናን ጉዳይ ነግሬያችሁ ሳበቃ ነው” ብሎ ለመናገር የፈለገውን ነገር ልባቸው እንደተንጠለጠለ ጨረሰላቸው፡፡
*   *   *
የሚያዳምጥ ህዝብ ማግኘት መታደል ነው፡፡ የሰማውን በልቦናው አሳድሮ ወደተግባር የሚለውጥ ህዝብ ማግኘት ደግሞ የመታደል መታደል ነው፡፡ ይህንን ለማግኘት ተጣጥሮ የአመለካከት ለውጥ ማምጣት ግድ ይላል፡፡ የለውጥ መንገዱ አዳጊ ሂደት እንጂ፤ በዚህ ጊዜ ለውጥ አመጣለሁ ብሎ ቀን ቆርጦ፣ መሳሪያ መርጦ በመቀመጥ የሚሆን አይደለም፡፡ ለውጥን ለማምጣት ለዋጩ ራሱ መለወጥ አለበት፡፡ የለውጡም ዓይነት መወሰን አለበት፡፡ ለውጡ ሥር - ነቀልና የመጨረሻው ዓይነት ከሆነ፣ ትራንስፎርሜሽን ነውና የቁርጡ ቀን ነው፡፡
የሥር - ነቀል ለውጥ ካደረገ፤ ከዚህ ቀደም የነበረው ምንነቱ ወዲያውኑ ተወገደ፣ ሞተ፣ ማለት ነው” ይለናል፤ ፈላስፋው ኤፒኩረስ፡፡
ሉክሩቲየስ የተባለው ሌላው ፈላስፋም፤
“ምንም ዓይነት ለውጥ ይሁን ለውጥ ከመጣ የቀድሞው ተንኮታኮተ፤ ስለዚህም ተደመሰሰ” ይላል፡፡ ይህ ማለት መሰረታዊ ለውጥ ተከስቷል እንደ ማለት ነው፡፡
ዞሮ ዞሮ በሀገራችን በኢትዮጵያ ለውጥ ይመጣ ዘንድ ከልባችን መመኘታችን አግባብነት አለው፡፡ ሁኔታዎች በአንድ ጊዜ ይከሰታሉ የሚል የዋህነት ግን አይኖርብንም፡፡ በየዘርፉ ያሉትን ችግሮች አንድ በአንድ በማየትና በመመርመር መላ ማበጀት ከጅምላ ዘመቻ ወይም ከሁሉን ባንዴ ርብርብ ያወጣናል፡፡ በሂሳብኛ አነጋገር integration by parts ብልት ብልቱን፣ በመጠን በመጠኑ እየቀመሩ ማዋሃድ እንደማለት ነው፡፡ የአገር አንድነትም መላው ይሄው ነው፡፡
ባለሙያዎቹን ወደ ስራውና ወደ ማዕዱ ማቅረብ ዋና ነገር ነው፡፡ አትሙት ላለው መላ አለው! ባለሙያ ሥራውን በፍቅር ይሰራ ዘንድ አዎንታዊ ድባብ (working atmosphere) ይፈልጋል፡፡ ቀዳሚው ፍቅር ነው፡፡ ከፍትፍቱ ፊቱን ይሻል፡፡ ውስጣዊ የሥራ ፉክክር ያወፍራል እንጂ አያቀጭጭም፡፡ መንፈስን ያጠነክራል እንጂ አያኮሰምንም፡፡ ይህም የአመለካከት ጉዳይ ነው፡፡ የበኩሌን ባዋጣ ሙሉው ስዕል ምሉዕነቱ ይረጋገጣል ብሎ የማሰብ ጉዳይ ነው፡፡ መማር የወረቀት ቀበኛ መሆን አይደለም፡፡ የሥራ መሰላል እንጂ፡፡ በመሰላሉ ጫፍ ወጣን ማለትም ሁሉን ቁልቁል እያዩ መኩራራት አይደለም፡፡ we shall never starve ብሎ የመቁረጥ ወኔ የሚፈልግ አያሉ የረሀብ ቢፌ እፊታችን ተደቅኗል! በጭራሽ ርሃብ አናማርጥም! ሁሉንም እናስወግዳለን እንጂ! መድኃኒቱ የየመስካችንን ኃላፊነት በቆራጥነት መወጣት ነው፡፡ እኔ ቆሜ ይህች አገር አትሸራረፍም ማለት ነው! ለዳተኝነት ቦታ አልሰጥም፣ ፍርሃት ደጄን አይረግጥም፣ አስፈላጊውን መስዋዕትነት ልከፍል ዝግጁ እሆናለሁ! ተበታትነን የትም አንደርስም! አጅ ለእጅ እንያያዝ! እንማከር፤ እንሰባሰብ፣ እንደራጅ!
“ካልተሳፈሩበት፣ ቶሎ ተሸቀዳድሞ፡፡
ጊዜ ታክሲ አይደለም አይጠብቅም ቆሞ!!
“የሚለውን አንዘንጋ! “ማነህ ባለሳምንት!” መባል አይቀርም፡፡ ያገኘነውን አጋጣሚ በወጉ መጠቀም ነው ብልህነት! አለበለዚያ፤ “ዕድለ-ቢስ ሰው፣ ግመል ላይ ተቀምጦ ውሻ ይነክሰዋል” የሚለውን ተረት እየተረትን፣ የሌሎች መጫወቻ ሆነን እንቀራለን፡፡ ምዕራባውያንና ምሥራቃውያን ወዳጆቻችን እንደ ወዳጅ የሚያስቡልን የሚመስሉት እስከጠቀምናቸው ድረስ ብቻ መሆኑን አንርሳ!   

የፌደራል ጠቅላይ አቃቤ ህግ ታዋቂውን የልብ ሃኪምና የአዲስ የልብ ህክምና ማዕከል ባለቤት ዶ/ር ፍቅሩ ማሩን ጨምሮ የ62 ተከሳሾች ክስ ትናንት ማቋረጡን አስታወቀ፡፡
ከቂሊንጦ ቃጠሎ ጋር በተያያዘ ዶ/ር ፍቅሩ ማሩን ጨምሮ የቀረበባቸውን ክስ እንዲከላከሉ በፍ/ቤት ከተበየነባቸው 38 ተከሳሾች መካከል 26ቱ ክሳቸው እንዲቋረጥ ተደርጓል፡፡
በእነ ማስረሻ ሰጠኝ የክስ መዝገብ ስር ከሚገኙት 38 ተከሳሾች መካከል አራቱ በሰው መግደል ወንጀል የተከሰሱ በመሆኑ ክሳቸው ባለበት እንዲቀጥል የተባለ ሲሆን ቀደም ሲል ስምንቱ ያህሉ በነፃ መሰናበታቸው ታውቋል፡፡
ቀሪዎቹ ክሳቸው የተቋረጠላቸው በተለያዩ የሽብር ወንጀሎች ተከሰው ጉዳያቸውን በማረሚያ ቤት ሆነው ሲከታተሉ የነበሩ መሆናቸው ታውቋል፡፡  

ዢ ጂፒንግ በወንዶች፣ አንጌላ መርኬል በሴቶች ቀዳሚነቱን ይዘዋል

    ታዋቂው ፎርብስ መጽሄት፤በ2018 የፈረንጆች አመት በተለያዩ መስኮች ተጠቃሽ አለማቀፍ ተጽዕኖ ፈጥረዋል ያላቸውን 75 የዓለማችን ሃያላን ዝርዝር ይፋ ያደረገ ሲሆን በወንዶች የቻይናው ፕሬዚዳንትና የኮሙኒስት ፓርቲ ዋና ጸሃፊ ዢ ጂፒንግ፣ በሴቶች የጀርመኗ መራሂተ መንግስት አንጌላ መርኬል ቀዳሚነቱን ይዘዋል፡፡
ላለፉት አራት ተከታታይ አመታት፣ የፎርብስ የአለማችን ቁጥር አንድ ሃያል ሆነው የዘለቁት የሩስያው ፕሬዚዳንት ቭላድሚር ፑቲን፤ዘንድሮ ቦታቸውን ለዢ ጂፒንግ አስረክበው፣ ወደ ሁለተኛ ደረጃ ዝቅ ያሉ ሲሆን የአሜሪካው ፕሬዚዳንት ዶናልድ ትራምፕ በሶስተኛነት ይከተላሉ፡፡
የአመቱ የአለማችን ቁጥር አንድ ሃያል ሴት የተባሉት የጀርመኗ መራሂተ መንግስት አንጌላ መርኬል፣ ከአለማችን ሃያላን የአራተኝነት ደረጃን መያዛቸውን የጠቆመው የፎርብስ መግለጫ፤ የአለማችን ቁጥር አንድ ባለጸጋ ጄፍ ቤዞስ አምስተኛ ደረጃ ላይ ተቀምጠዋል፡፡
የሮማው ሊቀ ጳጳስ ፍራንሲስ፣ የማይክሮሶፍቱ መስራች ቢል ጌትስ፣ የሳዑዲው ልዑል ሞሃመድ ቢን ሳልማን አል ሳኡድ፣ የህንዱ ጠቅላይ ሚኒስትር ናሬንድራ ሞዲና የጎግል ኩባንያ መስራች ላሪ ፔጅ እንደ ቅደም ተከተላቸው፣ ከስድስተኛ እስከ አስረኛ ያለውን ደረጃ ይዘዋል፡፡
በዘንድሮው የፎርብስ የአለማችን ሃያላን ዝርዝር ውስጥ 17 ሰዎች ለመጀመሪያ ጊዜ የተካተቱ ሲሆን፣ ተራማጅ እንደሆኑ የሚነገርላቸው የሳዑዲ አረቢያው ልዑል ሞሃመድ ቢን ሳልማን አል ሳኡድ፣ ከእነዚህ አዲስ ገቢዎች አንዱ ናቸው፡፡
በአመቱ የአለማችን ሃያላን ዝርዝር ውስጥ ከተካተቱ ታዋቂ ግለሰቦች መካከል 13ኛ ደረጃን የያዘው የፌስቡኩ መስራች ማርክ ዛከርበርግ፣ 36ኛ ደረጃን የያዙት የሰሜን ኮርያው መሪ ኪም ጁንግ ኡን፣ 66ኛ ደረጃን የያዙት የአፍሪካ ቁጥር አንድ ቢሊየነር ናይጀሪያዊው አሊኮ ዳንጎቴ እና 73ኛ ደረጃን የያዙት የአሸባሪው ቡድን አይሲስ መሪ አቡበከር አል ባግዳዲ ይገኙበታል፡፡
ፎርብስ የፖለቲካ ተጽዕኖ ፈጣሪነት፣ ተሰሚነት፣ የሃብት መጠን፣ የስኬት ደረጃና የመሳሰሉትን መስፈርቶች በመጠቀም ከገመገማቸውና በዝርዝሩ ውስጥ ካካተታቸው የአመቱ ሃያላን መካከል የአገራት መሪዎች፣ የኩባንያ ባለቤቶችና የስራ ሃላፊዎች፣ የተቋማትና ቡድኖች መሪዎች ወዘተ ይገኙበታል፡፡