Administrator

Administrator

Saturday, 07 April 2018 00:00

የተራራው ላይ ዛፎች ምኞት!

ካልጠፋ ሁሉ ከምድር
እንዴት ይገዟል የገባር ፣
በሔዋንማ በናታችሁ
ግንደ በል ነበራችሁ፡፡ (ዘፍጥ 3፣6) (… ወዳጄ ልቤና ሌሎችም … ገጽ 36 … ዛፍ በልታችሁ እንደሞታችሁ … በዛፍ ደግሞ ዳናችሁ! … ሲሉ አስተማሩን!)
*   *   *
በተራራው አናት ያሉ 3 ዛፎች ገና እንደተተከሉ፣ በችግኝ ዘመናቸው ሲወያዩ…. ተስፋቸውንና ህልማቸውን ሲነጋገሩ ለሰማቸው በጣም ይገርሙ ነበር፡፡ ከበታቻቸው ባለው ጥቅጥቅ ደን ውስጥ ካሉት ዘመዶቻቸው በተለየ መልኩ የተለየ ህልምና ምኞት ነበራቸው …  
*   *   *
የመጀመሪያ ዛፍ ችግኝ እንዲህ አለ … ‹‹.. እንግዲህ የሆነ ቀን አድጌ ስቆረጥ የከበሩ ዕቃዎች ማስቀመጫ እንዲሰሩብኝ እመኛለሁ፡፡ ዘናጭና ምርጥ በዓለም ካሉት ነገሮች ሁሉ የከበረ ነገር ማስቀመጫ ሳጥን መሆን ምኞቴ ነው፡፡ ይህ ካልተሳካልኝ ምኑን ኖርኩት … እኔ በተስማሚ ሁኔታ ለማደግ እሞክራለሁ … ቀሪውን ተካይና ተንከባካቢያችን ይጨነቅበት…››
ሁለተኛው ችግኝ እንዲህ አለ ‹‹…እኔ ግን ወደፊት የሆነ ግዜ ታላቅ መርከብ እንዲሰራብኝ እመኛለሁ፡፡ ምርጥና ውብ እንዲሁም ጠንካራ መርከብ ሆኜና ከንጉሶች ሁሉ ታላቅ የሆነውን ንጉስ ጭኜ በዓለም ዙሪያ መዞር … በእኔ ጥንካሬ ሰዎች ሁሉ እንዲተማመኑብኝና በእኔም መልካም ነገር እንዲሰሩብኝ እመኛለሁ …››
ሶስተኛው ዛፍ እንዲህ ሲል ምኞቱን አስቀመጠ ‹‹… እኔ የምመኘው በጣም ትልቅ፣ ረጅምና መለሎ ሆኜ ማደግ ነው፡፡ ሰዎች ሲመጡ ገና ከሩቁ ያዩኝና ይህስ ወደ መንግስተ ሰማያት ሊደርስ ምን ቀረው! እያሉ ያደንቁኛል፡፡ ከዛፎቹ ሁሉ ድንቅ እሆናለሁ፣ እናም ሰዎች በድንቅነቴ ያስታውሱኛል … ሲያስታውሱኝም … ‹… ያ! ዛፍ የሰማይ መክፈቻ ቁልፍ ቢኖረው ከፍቶ በገባ ነበር … ዳመናዎችን ወሽሟል … ዝናብን ይስማል …› …. ይሉኛል …››
ለምኞታቸው መሳካትም በየዕለቱ መትጋት ጀመሩ …
*   *   *
ከአመታት ጸሎት በኋላ ህልሞቻቸው እውን የሚሆንበት ወቅት መጣ፡፡ እነሆ በአንድ የጸደይ ማለዳ ጥቂት ዛፍ ቆራጮች ተሰብስበው ወደ ተራራው መጡ፡፡ አንደኛውም ወደ መጀመሪያው ዛፍ እየተጠጋና ግንዱን እየደባበሰው እንዲህ አለ …
‹‹ይህ ጠንካራ ዛፍ ይመስላል ስለዚህ ለአናጺው ወዳጃችን እንሸጥለታለን፡፡ እርሱም ሳጥን ይሰራበት ይሆናል…›› እናም መጥረቢያውን ይዞ ይቆርጠው ጀመር፡፡ ዛፉም እየተቆረጠ … ደስ አለው፡፡ ትክክል! እንደ ምኞቴና ህልሜ አናጺው የከበሩ ዕቃዎች ማስቀመጫ ሳጥን አድርጎ ይሰራኛል ሲል አሰበ፡፡
ሁለተኛውን ዛፍ እየደባበሰ ሌላው ዛፍ ቆራጩ እንዲህ አለ … ‹‹ይህም ጠንካራ ዛፍ ይመስላል፤ ይህንን ደግሞ ለመርከብ ሰሪው እሸጠዋለሁ… ጥሩ መርከብ የሚገነባበት ይመስለኛል …›› ሁለተኛውም ዛፍ እጅግ ደስ ብሎት ነበር፡፡ እነሆ ታላቅ መርከብ ሊገነባብኝና በመጨረሻም ህልሜ እውን ሊሆን ነው ሲል አሰበ፡፡
ወደ ሶስተኛው ዛፍ ሲመጡ ዛፉ በድንጋጤ ይንቀጠቀጥ ነበር፡፡ ቁመቴ ገና ሁሉን የሚበልጥ እጅግ ግዙፍ አልሆንኩምና አሁን ከቆረጡኝ ህልሜ አይሳክልኝም ሲል አስቦ ነበር፡፡ ከዛፍ ቆራጮቹ አንዱ እንዲህ አለ፡- ‹‹ከዚህ ዛፍ ምንም የተለየ ነገር አላየሁበትም፤ ሆኖም ቆርጬ ልውሰደው… መቼም ለሆነ ነገር ማገልገሉ አይቀርም…!›› አለና ቆረጠው፡፡
እነሆ ዛፎቻችን ተቆረጡ፤ ተጫኑ፤ ወደ ሰፈሩም ተጋዙ፡፡
የመጀመሪያውም ለአናጺው ተሰጠ፡፡ በእርግጥም አናጺው ሳጥን ሰራበት፡፡ ሆኖም ሳጥኑ የተሸጠው ለከበሩ ዕቃዎች ማስቀመጫ እንዲያገለግል ሳይሆን በበረት ውስጥ ለበጎች መመገቢያ ነበር፡፡ ዛፉም… ለዚህ አልነበረም የጸለይኩት ሲል አሰበና አዘነ፡፡
በሁለተኛውም ዛፍ የመርከብ ሰሪው ትንሽዬ የአሳ አስጋሪዎች የሚጠቀሙበት ታንኳ ሰራበት። ታላቅ መርከብ የመሆን ምኞቱ ድቅቅ አለ፡፡ ሆኖም ምን ይደረጋል! ሲል አሰበ፡፡ መርከብ መሆኔ ቢቀር … ታንኳም ቢሆን ሆኜ ልኑር የወደፊቱ አይታወቅምና…  ሲል ተቀበለው፡፡
ሶስተኛው ዛፍ ግን በረጃጅሙ እንደተቆረጠና ጥቂት እንደተስተካከለ ምንም ነገር ሳይሰራበት ከቆራጩ ዕቃ ቤት ተቀመጠ፡፡ እነሆ ወደ ጨለማው ዕቃ ቤት ተጣለና አቧራውን እየለበሰ … አዝኖ ቁጭ አለ፡፡ ተፀፀተ…
‹ምነው ጥቂት ጊዜ ቢተውኝ ኖሮ … ሁሉንም በልጬ አድግ ነበር!› ሲል አሰበ….
አመታት ነጎዱ፡፡ ዛፎቹም ህልማቸውን ዘንግተውና ረስተው መኖር ጀመሩ፡፡ ጸጥ ብለው ስራቸውን ይሰሩ ነበር፡፡ ከዕለታት በአንዱ ቀን ግን አንዲት ሴትና አንድ ሰውዬ ወደዚያ የበጎች በረት መጡ፡፡ ሴትየዋም በምጥ ተይዛ ነበር፡፡ ቆይታም ወንድ ልጅ ወለደች፡፡ ህጻኑንም ከመጀመሪያው ዛፍ በተሰራው በበጎቹ የመመገቢያ ሳጥን ውስጥ አስተኙት፡፡ እነሆም የመጀመሪያው ዛፍ ከዓለም ድንቅ ነገሮች ሁሉ የላቀው ድንቅ ማረፊያ ሆነ። በቤተልሄም ከተማ የከብቶች ግርግም የኖረ ቢሆንም፣ የዓለምን ታላቅ ስጦታ አቀፈ፡፡ አማኑኤልን፡፡
(የማቴዎስ ወንጌል 2፣ 1 -)
*ከሌላ ዓመታት በኋላ በሁለተኛው ዛፍ በተሰራው ታንኳ ሆነው ባህሩን ያቋርጡ ዘንድ ሰዎች ነበሩ … በባህሩ ላይ ታላቅ መናወጥ ሆነ፣ ታላቅ ማዕበልም ተነስቶ ታንኳይቱን ያንገላታት ያዘ፡፡  ያቺ ትንሽ ታንኳ ታላቁን ወጀብ ተቋቁማ ሳትሰባበር ታገለች፡፡ ከመካከላቸውም አንዱ ተነስቶ ‹‹ሰላም ይሁን!›› ብሎ ወጀቡንና ንፋሱን ገስፆ እስኪያቆመው ድረስ ያቺ ታንኳ ታላቅ ስራ ሰራች። ያ የተሸከመችውና ወጀቡን የገሰፀው ሰውም የንጉሶች ሁሉ ንጉስ የሆነው መሆኑን ባወቀች ግዜ ተደሰተች፡፡ እኛም የሁለተኛው ዛፍ ምኞት መሳካቱን አወቅን ….
(የማቴዎስ ወንጌል 8፣ 23 -)
*በመጨረሻም ከሶስተኛው ዛፍ ተቆርጦ ወደተቀመጠበት ጭለማ ክፍል አንድ ሰው መጣ፡፡ እነዚያን ቀጥ ያሉ የሶስተኛው ዛፍ ግንዶች አወጡ … መስቀልያ ሰርተውም ካጣመሯቸው በኋላ ለአንድ ምስኪን ሰው አሸክመው ያንገላቱት ጀመር፡፡ ስምኦን የተባለው የቀሬና ሰው ሲመጣ በእርሱ አህያ ጭነው ከዚያ የወጀብና የማዕበል አዛዥ ኋላ አስከትለው አስጓዙት፡፡ዋይ ዋይ የሚሉ እናቶች በሞሉበት መንገድ አቋርጠው ሲሄዱ ሰውየው ‹ለራሳችሁ አልቅሱ!› እያለ ይመክራቸው ነበር … ሰውየው በደም አበላ ታጥቦና በስቃይ ውስጥ ሆኖ ይጓዝም ነበር … ከቀራንዮ ተራሮች ላይ አወጡና በመስቀሉ ላይ ከሁለት ወንጀለኞች መሃል  ቸነከሩት፡፡
(የሉቃስ ወንጌል 23፣ 25 -)
ሶስተኛውም ዛፍ አለ ‹‹ … እነሆም በመጨረሻው በታላቁ ተራራ ላይ ታላቁን የሰማየ ሰማያት ልጅ ተሸከምኩ!... ምኞቴም ልክ መጣ … የሰማያትን ሁሉ መክፈቻ ቁልፍ በእኔ ላይ አኑረዋልና … ›› ሲል አሰበ፡፡
*   *   *
እንግዲህ የህልማችንን መፈቻ ወቅት መጠበቅ ግድ ነው … ለህልማችንም መሳካት መስራትና ቀሪውን ለተተኪያችን መተው ይገባል፡፡ የተመኘሁት አልተሰጠኝም፣  በወቅቱም አላገኘሁትም ልትል ትችላለህ፡፡  እመነኝ ላንተ የተባለ ዘግይቶም ቢሆን ወዳንተ ይመጣል፡፡
ዘግይቶም ቢሆን ግን በጣም ይፈጥናልና አይዘገይም፡፡
በርትቼ ብነሳ አውርጄም ባየው
ለካ ምግብ ኖሯል የተሰቀለው … (የሉቃስ ወንጌል 22፣ 19) (…ወዳጄ ልቤና ሌሎችም … ገጽ 69)
*   *   *
 (…የሃሳቡ አመንጪና እውነተኛ ፀሃፊው ያልታወቀ ሰው፡፡ ተሻሽሎ የተተረጎመ የ3ቱ ዛፎች ታሪክ …)
መልካም የትንሳኤ በዓል!

 “ማንነታችን እንዳንለያይ ሆኖ የተሰናሰነ፣ እንዳይነጣጠል ሆኖ የተገመደ፣ የተዋደደና የተዋሃደ ነው”

     የኢትዮጵያ አዲሱ ጠ/ሚኒስትር ዶ/ር አብይ ንግግር፤ ሁሉን ያስደነቀ በአንጻሩ ለተግባራዊነቱ ሁሉም ኢትዮጵያውያን ጉጉትና ተስፋ ሰንቀው በአንክሮ፣ እንዲከታተላቸው ያደረገ ነው፡፡ በበዓለ ሲመታቸው ቀን ያደረጉት ንግግርና የአቀራረብ ሰብዕና፤ ከፍተኛ ተቀባይነት ካገኙት መሪዎች ተርታ ያሰልፋቸዋል ለማለት ያስደፍራል፡፡ በመጀመሪያ የዳሰሷቸውን ሀሳቦችና ያሄሷቸውን ርዕሰ ጉዳዮች አንድ በእንድ እየነቀሱ ማየት ተገቢ ነው፡፡ ብዙዎች እንደሚያስታውሱት፤ ዶ/ር አብይ በጨው የተቀመመ፣ የሰውን ልብ የገዛ፣ የተስፋ ‹‹ገበታ›› ነው በንግግራቸው ያቀረቡት፡፡ የኢትዮጵያ ገበታ ሰፊ ነው እንዳሉት፣ እሳቸው ሰፊውን ገበታ ነው ለኢትዮጵያ እነሆ ያሉት፡፡
የአዲሱ ጠ/ሚኒስትር ዶ/ር አብይ ንግግር፤ ብዙዎችን የሳበበት ትልቁ ምክንያት የንግግሩ ማጠንጠኛ  የተቋጠረበት የትንታኔ ፍሰት ነው፡፡ የንግግራቸው ጅረት የተቀዳው ከተለያዩ ምልከታዎች በመሆኑ የብዙዎችን ትኩረት ስቧል፡፡ የሕዝቡን፣ የፓርቲውንና የጊዜውን እንዲሁም የወጣቱንና የጥቅል ማሕበረሰቡን የፍላጎት አውድ መሰረት አድርጎ የተነሳ በመሆኑም አድናቆት አትርፏል፡፡
 1ኛ. ኢትዮጵያዊ ፍልስፍናቸው የሚክስ ነው
በንግግራቸው ውስጥ ያቀረቡት የታሪክ ትንታኔያቸው፤ ለኢትዮጵያውያን ካሳ የከፈሉበት ነው ማለት ይቻላል፡፡ የኢትዮጵያን ታሪክና ማህበራዊ ስሪት ከተጨባጭ ሁኔታዎች ጋር አቆራኝተው መግለጻቸው፣ አንድ የንግግራቸው ጥንካሬ ይመስለኛል። ኢትዮጵያዊነትን  ትልቅ ቦታ ሰጥተው፣ ዋጋ የከፈሉ አባቶችን እውቅና መስጠታቸው ለአብዛኛው ኢትዮጵያዊ ትልቅ ካሣ የከፈሉበት ንግግር ነው፡፡ ከልዩነት አንድነትን አስቀድመው፣ በዚያው ደግሞ አንድነት፤ አንድ ዓይነትነት አይደለም ሲሉ የተደመጡበት ንግግራቸው መሳጭ ነበር፡፡ የሚፈልጉትን ሃሳብ  የገለጹበት ሞገስና  ትህትና፣ ንግግራቸውን አጣፍጦላቸዋል፡፡ ኢትዮጵያንና የሕዝቦቿን ጥምረት ሲገልጡ፤ ‹‹ማንነታችን እንዳንለያይ ሆኖ የተሰናሰነ፣ እንደይነጣጠል ሆኖ የተገመደ፣ የተዋደደና የተዋሃደ ነው፡፡›› ብለዋል፡፡ የማርቲን ሉተር ኪንግ ጁኒየርን፤ “I have a dream” ዓይነት ንግግር ይመስላል፡፡ መተማን፣ ካራማራን፣ ባድመንና አድዋን ሲያነሱ፤ ሉተር ሚሲሲፒን፣ ጆርጂያን፣ ቴኔሲንና የመሳሰሉትን እየጠቀሱ የተናገሩትን ይመስላል፡፡
2ኛ. አሳታፊ የሆነ የፖለቲካ ፍልስፍናቸው
ጥሪ ደማቅ ነበር
 ይህ ፍልስፍናቸው የሚቀዳው ምናልባትም ስለ ኢትዮጵያ ካላቸው እውቀት፣ የስራ ልምድ እንዲሁም ወጣትነታቸው ካቀበላቸው ስንቅ ሊሆን ይችላል። በመጀመሪያ ቁስል እንዳለብን ተገንዝበው የቁስል መፈወሻ ቃል ማቀበላቸው ያስደንቃል፡፡ ተቃዋሚ የሚለውን ተፎካካሪ፣ “ህገ መንግስቱን ለመናድ” የሚል ቅጥያ ስም የወጣላቸውን፣ ለሃገራችን በጎ ርዕይ ያላቸው ወንድሞቻችን፣ ጽንፈኛ ዲያስፖራ የሚለውን፣ ኢትዮጵያን በውስጣቸው ይዘው የሚዞሩ አፍቃሪ ኢትዮጵያውያን ሲሉ ቁስሉን ሽረውታል፡፡ በተዘዋዋሪ ነፍጥ አንስተው ከተለያዩ የኢትዮጵያ ጠላቶች ጋር ሲዋደቁ የኖሩትን አርበኞች እውቅና መስጠታቸው ያስደንቃቸዋል፡፡ ኢትዮጵያ፤ ከኢህአዴግም ሆነ ከሌሎች የፖለቲካ ድርጅቶች በላይ መሆኗንም ተናግረዋል - ‹‹ኢትዮጵያ ከፖለቲካ አመለካከት በላይ ነች›› በማለት። ይህ ምን ማለት ነው? “ኦህዴድ ወይም የፖለቲካ መስመሩ ከኢትዮጵያ አይበልጥብኝም” እንደ ማለት  ነው፡፡ ይህ ነው አዲሱ መንገዳችን የሚሉም ይመስላል፡፡ ከአብዮታዊ ዴሞክራሲ እውነትና “የኔ ብቻነት” የተላቀቁ መሆናቸውን ንግግራቸው ይጠቁማል፡፡ ድርጅቱንም ወደዚህ ጠርዝ ፈቀቅ ያደርጉታል ብሎ መገመት ይቻላል።
3ኛ. ዴሞክራሲንና ፍትህን ከነጻነት
ጋር አንስተው ያሄሱበት ንግግር ይለያል
በንግግራቸው ውስጥ የዴሞክራሲን አስፈላጊነት ብቻ ሳይሆን ተግባራዊነቱን ፈትሸዋል፡፡ አገሪቱ በተስፋና በስጋት ውስጥ ናት ሲሉ ከተናገሩ በኋላ ምክንያቱን ሲዘረዝሩ፤ የዴሞክራሲ እጥረት ነው ብለዋል፡፡ ግለሰቦች ነጻነታቸው ተገድቧል ሲሉ በግልጽ ተናግረዋል፡፡ በአጭሩ የዲሞክራሲ ሥርዓቱን የተቸ የሰላ ሃሳብ አቅርበዋል፡፡ ነጻነት የተፈጥሮ ጸጋ እንጂ የመንግስት ሥጦታ አይደለም ብለዋል - ጠ/ሚኒስትሩ፡፡ በዚህም ከቡድን  ነጻነት ይልቅ ለግለሰብ ነጻነት ቅድሚያ (ትኩረት) መስጠታቸውን መገንዘብ አያዳግትም፡፡ ይህም ኢህአዴግን ወደ አዲስ መንገድ  ይመሩታል የሚል ሃሳብ ያጭራል፡፡አዲሱ ጠ/ሚኒስትር፣ ማልኮም ኤክስ እንዳለው፤ “we haven’t benefited from America’s democracy, we suffered from America’s hypocrisy” (ከአሜሪካ ዴሞራሲ እየተጠቀምን ሳይሆን በግብዝነቱ እየተሰቃየን ነው) የሚለውን ዓይነት ሃሳብ ማንጸባረቃቸው ያስደምማል፡፡
4ኛ. የተዘነጉ የሕብረተሰብ ክፍሎችን በተገቢ ሁኔታ ያስታወሰ ንግግር
የተዘነጉ የሕብረተሰብ ክፍሎችን ለፖለቲካ ትርፍ ሳይሆን ለተጠቃሚነታቸው መስራት እንደሚገባ ተናግረዋል፡፡ ለምሳሌ የወጣቱን ክፍል ሃሳብ፣ጥያቄና ትግል እውቅና ሰጥተዋል፡፡ ተግባር ሲጨመርበት ደግሞ የግሩም ግሩም ይሆናል፡፡ ሌላው ያነሱት የሴቶችን ትግል አስፈላጊነት ነው፡፡ የሴቶች ትግል በትክክል ሊወከል እንደሚገባው ተናግረዋል፡፡ ዶ/ር አብይ በንግግራቸው መደምደሚያ ላይ የእናታቸውን፣ የሚስታቸውንና የሌሎች እናቶችን ሚና በሚገባ ማንሳታቸው፣ ቁርጠኛ የሴቶች መብት ተሟጋች ያደርጋቸዋል፡፡ ምናልባትም የእናታቸውን ውለታ እያዩ አድገው፣ የኢትዮጵያውያንን እናቶች ጭቆና አስተውለውና የወለዷቸው ሦስት ሴት ልጆች ዕጣ ፈንታን ተገንዝበው ትኩረት የሰጡት ጉዳይ ስለሚመስለኝ፣ ከንግግራቸው ትልቁን ቦታ የሚይዝ ሊሆን እንደሚችል እገምታለሁ፡፡ “Which side of America are you living in” እንደተባለው፤ኢትዮጵያ ውስጥ ያለውን የአኗኗር ሁናቴ አጢነው፣ በዚህ አቅጣጫ ለውጥ ለማምጣት የፈለጉ ይመስላሉ፡፡ ድሃ አደጉን አይተውታል፡፡ የእናቶችን፣ የባልቴቶችንና ሕጻናትን ሁኔታ ያውቁታል፡፡
4ኛ. የማህበራዊ ፈውስ (ሶሻል ቴራፒ) ፈጣን መርሃቸው ይመስላል
የንግግራቸው አንኳር ማጠንጠኛው፤ ማሕበራዊ ፈውስ ነው፡፡ አንዳንድ ሰዎች ስለ ኢትዮጵያ ያላቸውን የተሳሳተና የተንጋደደ አስተሳሰብ በተመለከተ እርምት ሰጥተዋል፡፡ ጨለምተኛነትንና ጠባብነትን እንዲሁም የታጋይ ግብዝነትን ተችተዋል፡፡ ኢትዮጵያ ዴሞክራሲያዊት አገር ናት ሲል ደምድሞ የተነሳውን ድርጅታቸውንም ቢሆን  ሞግተውታል፡፡ በመጀመሪያ ለሰብአዊ መብት ሲሟገቱ፣ ህይወታቸውን ለተነጠቁ  ግለሰቦች ይቅርታን ጠይቀዋል፡፡ ይህ ትልቅነት ነው። ፈውስ ያመጣል፡፡ ይህን በማለታቸው ጠ/ሚኒስትሩ ከድርጀታቸው ያፈነገጡ የሚመስላቸው አይጠፉም። ግን አፈንግጠው አይደለም፡፡ ብዙዎቹም የድርጅቱ አባላትም ይህን ይጋሯቸዋል፡፡
የሙሰኞችን የበረታ እጅ አንስተው ፍትሃዊ የሃብት ክፍፍል እንደሌለ አስምረውበታል፡፡ አንዱ ዘርፎ አንዱ ሰርቶ የሚኖርባት አገር ማየት አንፈልግም ብለዋል። ‹‹የልዩ ተጠቃሚ ነን” ኃይሎችንና ወደፊት አዳዲስ ጎሳን ወይም ሌላ የጥገኝነት መስመር ዘርግተው፣ ለዘረፋ የተዘጋጁ ተስፈኞችን፤ ድርጅታቸውንና ሰፊውን ሕዝባቸውን ይዘው እንደሚታገሏቸው መግለጻቸው ያስደንቃል። የማሕበራዊ ማለትም የፖለቲካ ተጽዕኖ፣ የኢኮኖሚ ብዝበዛና በአዲስ መልክ የተገለጸውን ዘረፋና ማሕበራዊ ውርደት (ሶሻል ዲግሬዲሽን) አውግዘዋል፡፡ ወደፊት እንደማይከሰትም ተስፋ ሰጥተዋል፡፡ ‹‹ሰርቆ አደሮች››፣ በሰርቶ አደሮች ይሸነፋሉ ማለታቸው ነው፡፡
ኢትዮጵያ ምንም ዓይነት ዕድገት አላሳየችም የሚሉትንም ጨለማ አንጋሾች በሥነ አመክንዮ ሞግተዋል፡፡በአንጻሩ ሰዎች በኢትዮጵያ ተስፋ እንዲሞሉ፣ ”ኢትዮጵያ ማሕጸነ ለምለም ናት” ሲሉ ተደምጠዋል፡፡ ተስፋ ነው፡፡ የትምህርት ጥራቱን አንስተው ሲናገሩም፤ “ጥራት የለም” ከሚሉ ብዙ ተችዎች ጋር አቀራርቧቸዋል። ይህም ማህበረሰቡን  የማድመጥ ችሎታቸውን ያሳያል። ጠ/ሚኒስትሩ ለትምህርት የሰጡት ቦታ ትልቅ ነው፡፡ ትምህርት ለነጻነት ያለውን አስተዋጽኦ ታላቁ የጥቁሮች ታጋይ ፍሬደሪክ ዳግላስ አጽኖት እንደሰጠው መሆኑ ነው፡፡
ይቅርታንና ፍቅርን ማንሳታቸው አንዱ የማህበራዊ ፈውስ ፈላጊነታቸውን ማሳያ ነው፡፡ አንዳንዶች ብሔራዊ እርቅ ሲሉት ሌሎች ብሔራዊ መግባባት ይሉታል። እሳቸው ግን ሦስተኛውን መንገድ መርጠዋል፡፡ ይቅርታ እና ፍቅር፡፡ ይቅርታ ሲሉ፤ በዳይና ተበዳይ አለ ማለታቸው ነው፡፡ ፍቅርን ሲያነሱ፤ ጠብ ወይም ቁርሾ አለ ማለታቸው በመሆኑ የቃላት ንትርኩን ትተው፣ የይቅርታ እና የፍቅር አስፈላጊነትን  ነው ያነሱት፡፡ በሌላ አነጋገር፤ ጠ/ሚኒስትሩ ተግባሩ ላይ ነው ትኩረት ያደረጉ የሚመስሉት፡፡ ለፍቅር ያላቸው ሃሳብ፣ ከደቡብ አፍሪካው ኔልሰን ማንዴላ ጋር ያመሳስላቸዋል፡፡”እምዬ ምኒልክ” እንዲሉ፣ “እምዬ ፍቅር” እንላቸው ይሆናል፤ማን ያውቃል!?
5ኛ. ተስፈኛነትና እራስን ማግኘትን
ያንጸባረቀ ንግግር   
ድርጅታቸውን ኢህአዴግን እንደሚወዱት ምንም ጥርጥር የለኝም፡፡ ባይሆን ኖሮ ይህን ያህል ጊዜ በድርጅቱ ውስጥ አይቆዩም ነበር፡፡ ይሁን እንጂ ለድርጅቱ ያላቸው ፍቅር፤ በድርጀቱ አስተሳሰብ  ሙሉ በሙሉ የሟሙ አላደረጋቸውም፡፡ ማልኮም ኤክስ፤ ‹‹እኔ አሁንም የእስልምና እምነት ተከታይ ነኝ፤ ከዚሁ ጋር የጥቁሮች ብሔርተኛ መሪ ነኝ፡፡ የኔ ሐይማኖታዊ ፍልስፍና እስልምና ነው፡፡ ለነብዩ መሐመድ ትልቅ ቦታ አለኝ፡፡ የፖለቲካና የኢኮኖሚ ፍልስፍናዬ፣ የጥቁር ብሔርተኝነት ነው፡፡›› እንዳለው ነው፡፡ ዶ/ር አብይ የኢኮኖሚ፣ የፖለቲካና የማሕበራዊ ፍልስፍናቸው፤የኢህአዴግ ዓይነት ቢሆንም ከአብዮታዊ ዴሞክራሲያዊ ፍልስፍና ሌላ የሃይማኖት ፍልስፍናቸው በግልጽ ነጥሮ የወጣበት ንግግር ነው ያቀረቡት፡፡
ለዚህ አንዱ ምስክር፤ እኔ ብቻ ወይም ለእኔ ብቻ ወይም ፓን ሰልፊዝም አያስፈልግም ብለዋል፡፡ ቃል በቃል ለማስቀመጥ፤ ‹‹የኔ ሃሳብ ብቻ ካላሸነፈ ሞቼ እገኛለሁ›› ማለትን ተችተዋል፡፡ የሪፐብሊካኑ እጩ ተወዳዳሪ ዶ/ር ካርሰን፤ የሪፐብሊካንን እና የዴሞክራትን “የኔ ይሻል፣ የኔ ይሻል” ደረቅ ሙግትን ሲተቹ፤  “My way or the Highway” ማለት አያስፈልግም እንዳሉት ማለት ነው፡፡ የአዲሱ ጠ/ሚኒስትር ፍልስፍና፤ መደማመጥ፤ መመካከር ይመስላል፡፡ በሌላ በኩል ደግሞ፤ ”ይህ ወይም ያኛው ፖሊሲ ወይም አዋጅ የሚለወጠው በኢህአዴግ መቃብር ላይ ነው” የሚለውን ግትር አቋም አሂሴው ነው ያለፉት - በንግግራቸው፡፡
ሌላው  የፈጣሪን ስም  ማንሳታቸው ካለፉት ሁለት ጠ/ሚኒስትሮች ይለያቸዋል፡፡ ይህ ደግሞ የፈሪሃ እግዚአብሔርን አስተሳሰብና የማሕበረሰቡ የሞራል መሪ ምስረታ ላይ ገንቢ ሚና ይኖረዋል፡፡ “ለምመራው ሕዝብ ስል የማምንበትን እምነት አልናገርም” ሲሉን እንደነበሩት መሪዎች፤ አብይ (ዶ/ር) ድብቅ አልሆኑም። የአዲሱ ትውልድ ትሩፋት ይህ ነው፡፡ ግልጽነት!!! የተግባር ፈፋውን ይሻገሩት ይሆን? እግዚአብሔር ይርዳቸው፤ ሰውም ይስጣቸው፡፡ የኦሮሞው ታሪክ ፀሃፊ ዓፅመ ጊዮርጊስ፤ “አቤቱ እባክህ ጌታዬ፤ ምኒልክን ከክፉ …ጠብቃቸው” እንዳለው፤ እኔም “አቤቱ  ጌታዬ፤ እባክህ አዲሱን ጠ/ሚኒስትር ከእንቅፋቶች ሁሉ ጠብቃቸው፣ መከናወንንም እንደ ታላላቆቹ መሪዎቻችን ስጣቸው፣ የታላላቆቹን መሪዎች ድካምንስ አርቅላቸው። ኢትዮጵያውያን እፎይ ብለው ይኖሩ ዘንድ!!” እላለሁ፡፡

 ተወዳጁ ሸገር 102.1 ኤፍኤም ሬዲዮ ጣቢያ፤ “ኢትዮጵያ ለዘለዓለም ትኑር” የሚለውን ቃል እንደ መፈክር በማስተጋባት ይታወቃል። ከመፈክርም በላይ ግን የጣቢያው መሪ ቃል ሆኗል፡፡ የሬዲዮ ጣቢያው የፕሮግራሞች መክፈቻና መዝጊያ ነው፡፡ በዚህም የተነሳ የሸገር ሬዲዮ ሌላ ስሙ እስከ መሆን ደርሷል - “ኢትዮጵያ ለዘለዓለም ትኑር”!! በሚያስገርም ሁኔታ ግን ሸገር ይሄን ቃል መጠቀሙ የማያስደስታቸው ወገኖች እንዳሉ የጣቢያው ሃላፊዎች ይናገራሉ። “የድሮ ሥርዓት ናፋቂዎች” ለሚል ፍረጃም ዳርጓቸዋል፡፡ “ይሄን ቃል ለምን እንደማይወዱት ግን አናውቅም” ይላሉ - ሃላፊዎቹ፡፡
እንዲያም ሆኖ ይህ በሸገር ለዓመታት ሲዘመር የዘለቀው “ኢትየጵያ ለዘለዓለም ትኑር” የሚል የመልካም ምኞት ቃል፣ በሬዲዮ ጣቢያው ብቻ ተወስኖ አልቀረም፡፡ ከቅርብ ጊዜ ወዲህ ብዙዎች የሚያዜሙት ቃል እየሆነ መጥቷል። አዲሱ የአገሪቱ ጠ/ሚኒስትርም ታሪካዊውን ንግግራቸውን የቋጩት በዚህ ቃል ነው፡፡ ሸገሮች ምን ተሰምቷቸው ይሆን? ለመሆኑ ቃሉን ለጣቢያቸው የመጠቀም ሃሳብ ከየት መነጨ? ምን ተግዳሮትስ ገጠማቸው? የአዲስ አድማስ ጋዜጠኛ አለማየሁ አንበሴ፤ ሸገር ሬዲዮን ከመሰረቱትና ከሚመሩት አንዱ የሆነውን አርቲስት ተፈሪ ዓለሙን በዚህ ዙሪያ አነጋግሮታል፡፡
             

    “ኢትዮጵያ ለዘለዓለም ትኑር” የሚለውን መሪ ቃል መጠቀም የጀመራችሁት እንዴት ነው?
 ከዛሬ 19 ዓመት በፊት በኤፍኤም አዲስ 97.1 ሬዲዮ ላይ የ”ጨዋታ” ፕሮግራምን በጀመርን ወቅት ፕሮግራማችንን ስናስተዋውቅ፣ ”ኢትዮጵያ ለዘለዓለም ትኑር” እንል ነበር፡፡ በመጀመሪያ የ”ጨዋታ” ፕሮግራምን ስናዘጋጅ ዝም ብለን ጀመርነው፡፡ ከዚያ በኋላ የፕሮግራማችን መሪ ቃል (Moto) አደረግነው፡፡
ጣቢያው ውስጥ ተነጋግራችሁበትና ተመካክራችሁበት ነው የጀመራችሁት?
አይደለም፡፡ ስለ ሀገር ጉዳይ በምናነሳ ወቅት በማሳረጊያችን በልማድ “ኢትዮጵያ ለዘለዓለም ትኑር” እንል ነበር፡፡ በኋላ ግን ለምን የፕሮግራማችን መክፈቺያና መዝጊያ አይሆንም ብለን ሲጀመርም ሲጠናቀቅም ቃሉን ወደ መጠቀም ገባን፡፡ በዚህ ሁኔታ እየተለመደ መጣና አጠናክረን ቀጠልንበት። በኋላ እንደውም ያልተገባ ትርጉም ሲሰጠው፣ እኛ አጠናክረን ነው  የቀጠልንበት፡፡ አሁን ግን ሸገር ላይ የምንጠቀምበት አውቀን፣ ሆን ብለን መሪ ቃላችን (Moto) በማድረግ ነው፡፡  
መሪ ቃሉን መጠቀም ከጀመራችሁ በኋላ የገጠማችሁ ተግዳሮት ነበር?
ብዙ ጊዜ ቃሉ እንዲባል አይፈለግም ነበር። በወቅቱ እንደውም አንድ የጣቢያው ኃላፊ፤ ”ኢትዮጵያ ለዘለዓለም ትኑር የምትሉት የምን መፈክር ነው? በመፈክር ሃገር አያድግም” ብለው አነጋግረውን ነበር። በወቅቱ እኔም፤ “ኢትዮጵያ ለዘላለም ብትኖር ምን ችግር አለው?” ብዬ ለመመለስ ሞክሬ ነበር፡፡ እሳቸው ግን “አይ ተፈሪ፤ ልክ እናንተ ቃሉን ስትሉት፣ ሀገሪቷ ላይ ችግር ያለ ይመስላል” ብለውኛል፡፡ ከዚህ ውጭ ሌሎች ለምን ቃሉን እንደማይወዱት አይገባኝም፡፡ ብዙ ጊዜ ደስ አይላቸውም ነበር፡፡ “የትኛዋ ኢትዮጵያ…?” ምናምን በሚል ለማጣጣል ነው የሚሞከረው፡፡ መቼም “የዚህኛው የዚያኛው መንግሥት ኢትዮጵያ” ማለት አይቻልም፡፡ ግን ቃሉ አይወደድም ነበር፡፡
ኃላፊዎች ከማነጋገር ባለፈ የወሰዱት እርምጃ የለም?
የለም፡፡ ዝም ብለው “ለምንድን ነው የምትጠቀሙት” ነበር የሚሉት፡፡ እኛም ክርክራችን፤ “ኢትዮጵያ ለዘለዓለም ብትኖር ችግሩ ምንድን ነው?” የሚል ነበር። ምናልባት እነሱ ድሮ የሚባል ነገር ስለሆነ እንዲሁ ቃሉ ከብዷቸው ሊሆን ይችላል፡፡ ግን ሃገር መውደድ ድሮም ነበር፤ አሁንም አለ፡፡ ለሃገር ጥሩ መመኘት ድሮ ኖሮ፣ አሁንም ብትመኝ ምን ችግር አለው? ብዙ ጊዜ ተፅዕኖ ነበር እንጂ ሌላ እርምጃ ውስጥ አልተገባም። አሁን በሸገር ላይ ያሉ ፕሮግራሞች በሙሉ ቃሉን ይጠቀሙበታል። በዚች ቃል ምክንያት “የድሮ ስርአት ናፋቂዎች” የሚሉ ፍረጃዎች መስፋፋት ጀምረው ነበር፡፡ ሆኖም “ውሾች ይጮሃሉ ግመሎች መንገዳቸውን ይቀጥላሉ” እንደሚባለው እኛም ቀጥለንበታል፡፡
ግን በታሪክ ይህን ቃል መጠቀም የተጀመረው መቼ ነው? ማንስ ጀመረው?
ድሮ ከአፄ ኃይለሥላሴ ጊዜ ጀምሮ በንግግሮች ማብቂያ ላይ የሚባል ልማዳዊ ንግግር ነው። ረጅም እድሜ ለንጉሡ ወይም ለጳጳሱ ማለት የተለመደ ነበር። በመጨረሻ ላይም ኢትዮጵያ በነፃነት ለዘለዓለም ትኑር! ይሉ ነበር፡፡ በጣም ጎልቶ መባል የተጀመረው እንደውም ከፋሽስት ወረራ በኋላ ነበር። ምክንያቱም ሃገር ያለመኖር ማለት ምን ማለት እንደሆነ በወቅቱ አይታወቅም፡፡ ከወረራው በኋላ ግን በብዙ ንግግር ውስጥ ይገባ ነበር፡፡ እኛም ያንኑ ነው የተጠቀምነው፡፡ ስለ ታሪክ፣ ስለ ማንነት እየተናገርን፣ በዚያው መጠን መደምደሚያችን ይሄ ቃል ነበር፡፡ አሜሪካኖቹም እኮ የራሳቸው የሚሉት፣ ስለ ሀገራቸው የሚግባቡበት የጋራ ቃል አላቸው፡፡
አዲሱ ጠቅላይ ሚኒስትር ዶ/ር አብይ፤ ይሄን ቃል ባልተለመደ መልኩ ተጠቅመውበታል …
ከአሁን በፊት የጅቡቲው ፕሬዚዳንት ኢስማኤል ኦማር ጊሌ፣ እዚህ መጥተው ንግግር ሲያደርጉ፣ ሁልጊዜ  ቃሉን ይጠቀሙበት ነበር፡፡ በአማርኛ ነበር ቃሉን የሚሉት፡፡ የቀድሞ ጠ/ሚ ያረፉ ሰሞንም፤ ኢትዮጵያ ለዘለዓለም ትኑር የሚለው ቃል፣ ከፎቶግራፋቸው  ጋር ተደርጎ  ይሸጥ ነበር፡፡
ዶ/ር አብይ በንግግራቸው መዝጊያ ላይ  ይሄን ቃል በመጠቀማቸው ምን ተሰማህ?
ለኛማ ደስ ነው የሚለን፡፡ ሁሉም ሰው ቢያስተጋባው መልካም ነው፡፡ ሁሉም እየተቀበለው ሲሄድ፣ ኢትዮጵያ ለዘለዓለም ትኑር መባሉ ልክ እንደነበርን ያረጋግጥልናል። ጠቅላይ ሚኒስትሩ ብቻ ሳይሆኑ ሁሉም ሰው ቢለው ደስ ይለኛል፡፡ የዕለት ፀሎታችን ቢሆን ደስ ይለናል። ለሀገራችን ያለንን ምኞት የምንገልፅበት ስለሆነ ቃሉ መልካም ነው፡፡

 የጠ/ሚ አብይን ንግግር በጽሞና አደመጥኩት። ታሪካዊ ንግግር ነው። ሲጠቃለል፣ ሰውየው በቃል የመፈወስ ተሰጥኦ አለው። አይተናል። ሰምተናል። ቀጥልበት እንለዋለን።
ከ27 ዓመት በኋላ ኢትዮጵያችን፣ በኢትዮጵያ ፓርላማ፣ በኢትዮጵያ መሪ በክብር ተዘከረች፣ የመጽናናትን ቃል ሰማች።
ኢትዮጵያ “መጪው ጊዜ የፍቅርና የይቅርታ ነው፤” ተዘጋጂ ተባለች። ድንቅ ነው።
ከመሪዎቿ መልካም ተግባርን ብቻ ሳይሆን መልካም ቃላትንም ተነፍጋ የሰነበተች አገር፤ በዚህ ንግግር በሐሴት ብትሞላ የሚያስደንቅ ሊሆን አይገባም። ሰው በምግብ ብቻ አይኖርም ተብሎ ተጽፏል። በአብይ ንግግሩ ቅር ሊሰኙ የሚችሉት ሰዎች ቢኖሩ በጣም ጥቂት ናቸው።
አሰባሳቢና ጋባዥ ንግግር ነው።
ለበዓለ ሢመት የተገባ፣ ጊዜውን የሚመጥን ንግግር ነው። (እርግጥ ከ35 ደቂቃ ማጠር ይችል ነበር። መሰል ንግግሮች የይዘት ዝርዝር ሳይሆን የመንፈስ ጉዳዮች ናቸው። አብይ ንግግሩን የገነባው በለውጥ፣ ተስፋና በአንድነት ዙሪያ ነው። ሁሉንም የንግግሩን ዘለላዎች እያነሣን ብንተነትን፣ ማሰሪያቸው የለውጥ ተስፋና አንድነት ሆኖ የምናገኘው ይመስለኛል። ስለ እናቱና ሚስቱ ባነሣበት የተዘክሮ ዘለላው ሳይቀር፣ ውለታቸውን በማስታወስ በኩል የሚጠራን ወደ ተስፋና ትብብር ነው። ኢትዮጵያውያን በየዳር ድንበሩ መሰዋታቸውን ያነሣበት አቀራረብም እንደዚያው ነው። ሌሎችም ይኖሩ ይሆናል። ያስቀመጠው የለውጥ ተስፋ የማያረካው ሰው ቢኖር፣ ስለ አንድነታችንና ስለ ጋራ ታሪካችን ያነሣው ያካክስለታል። በተገላቢጦሹም እንደዚያው። እንደ ቀዳሚዎቹ መሪዎች የኢህአዴግን ስኬቶች በማጋነን አልተጠመደም። እያንዳንዱን ስኬት ጠቅሶ የሚያስከትለው ጎዶሎ እንደነበረና ለውጥ እንደሚያስፈልገው ነው።
የአብይ ንግግር የሚለየው በአቀራረቡ ብቻ ሳይሆን በመንፈሱም ነው።
የራሱ የንግግር/አጻጻፍ ስልትም በጉልህ ተለይቶ የሚታይ ነው። እንደ ጭብጥ ብቻ ካየነው ግን ጥቂት የማይባሉትን ጭብጦቹን በሁለቱ የቀድሞ ጠ/ሚኒስትሮች ንግግሮች ውስጥ የምናገኛቸው ናቸው። --- ጊዜው ያላቸው ሰዎች በስፋት ቢተነትኑት እመኛለሁ። ማሰሪያው ግን ተስፋው ወደተግባር የሚለወጥበትን ፍኖተ ካርታ ማቅረብ ነው። አብይ በቀጣዮቹ ቀናት፣ ቢበዛ ሳምንታት ውስጥ ዋና ዋና የትግበራ አቅጣጫዎቹን ማሳወቅ ይኖርበታል። የአፍህን ሰማን፤ እጅህ ከምን?!
መልካም ዕድል፣ ኢትዮጵያችን
(መስፍን ነጋሽ - ከፌስቡክ)

 ታሪካዊ እንደሆነ የተነገረለት የአዲሱ ጠቅላይ ሚኒስትር ዶ/ር አብይ አህመድ ንግግር ባልተለመደ መልኩ አብዛኛውን የህብረተሰብ ክፍል አስደስቷል፡፡ ተቃዋሚዎችን ጨምሮ፡፡ ምስጢሩ ምንድን ነው? ከንግግራቸውም በመነሳት ብዙዎች ለጠ/ሚኒስትሩ ድጋፋቸውን ሰጥተዋል፡፡ የአዲስ አድማስ ጋዜጠኛ አለማየሁ አንበሴ ፖለቲከኞች፣ የሃይማኖት አባቶችና ታዋቂ ኢትዮጵያውያን በጠ/ሚኒስትሩ ንግግር ላይ ያላቸውን አስተያየት አሰባስቦ እንደሚከተለው አጠናቅሮታል፡፡


               “ስለ ኢትዮጵያና ስለ ወላጅ እናታቸው ሲናገሩ አንብቻለሁ”
                  አባ ገዳ በየነ ሰንበቶ (የኦሮሞ አባገዳዎች ም/ቤት ሰብሳቢ)

    በእውነት ዶ/ር አብይ ከአንድ ኢትዮጵያዊ የሚጠበቀውን ንግግር ነው ያደረጉት፤ አንጀት የሚበላ ነው፡፡ የተራራቀውን ህዝባችንን የሚያቀራርብ ነው፡፡ ከአንድ መሪ የሚያስፈልገውም ይሄ ነው፡፡ የኢትዮጵያ ህዝብም የተጠማው ይህን አይነቱን ውስጥን የሚያለመልም፣ ተስፋ የሚሰጥ፣ ትህትና የተሞላበትን ንግግር ነበር፡፡ እኛም እንደ አባ ገዳና ሃገር ሽማግሌ ስንመኝ የነበረው፣ እንዲህ ሃገሩን ከፍ አድርጎ የሚጠራ መሪን ነው፡፡ ቋንቋችን ዥንጉርጉር ይሁን እንጂ ደማችን አንድ ነው ብዬ ደጋግሜ ተናግሬያለሁ፡፡
ከዚህ በኋላ የሚፈለገው የተናገሩትን ወደ ተግባር እንዲለውጡልን ነው፡፡ መናገሩ ብቻ ሳይሆን ዋናው ተግባሩ ነው፡፡ ወደ ተግባር እንደሚለውጡት ደግሞ እተማመናለሁ፡፡ ከአንዲት ኢትዮጵያዊት የተወለደ፣ ከአንድ ኢትዮጵያዊ የተወለደ፣ ኢትዮጵያዊነቱን ያልዘነጋ፣ የተጣላን የሚያስታርቅ፣ ከሃገር የወጣውን የሚያስመልስ፣ ጫካ የገባውን ወደ ሃገሩ በፍቅር የሚመልስ መሪ እንዲሆኑ ነው ፈጣሪን የምንለምነው፡፡ እኔ በበአለ ሲመቱ ላይ ነበርኩ፤ እውነቴን ነው የምልህ በጣም ነው ያለቀስኩት፡፡ ንግግሩ ነው ያስለቀሰኝ፡፡ ከኢትዮጵያዊነታችን ጋር ነው የተገናኘነው፡፡ ሰው በጎሳ ተከፋፍሎ ሲተራመስ የነበረበትን ጊዜ እያስታወስኩ ነበር ያለቀስኩት። ለወደፊትም ይህቺን ሃገር ለማዳንና ለትውልዱ ለማስረከብ የሚያስፈልገው እንዲህ ያለው መሪ ነው፡፡ አንድ ኢትዮጵያዊ መሪ የሚጠበቅበት ይህ ነው፡፡ እኔ ደስ ብሎኛል፡፡
ስለ ወላጅ እናታቸው ሲያነሱ አንብቻለሁ፡፡ እናታቸውን ሲያነሱ የሁሉንም እናት እንዳነሱ ነው የተረዳሁት፡፡ ስለ ኢትዮጵያና ኢትዮጵያዊነታችን ደጋግመው ሲናገሩ፣ ብዙ ነገር ነው የተሰማኝ። በሌላ በኩል ደግሞ በሃገር ውስጥም በውጪም ካሉት ጋር እንሰራለን ሲሉ፣ በሆዴ ውስጥ ትኩስ ወተት ነው ሲፈስ የተሰማኝ፡፡
እኛ መደማመጥና መተባበር ስንችል ነው ቃላቸው ወደ ተግባር የሚለወጠው፡፡ ስለዚህ መደማመጥ መቻል አለብን፡፡ ጊዜ መስጠት አለብን። መተባበርና መደጋገፍ፣ የተሳሳቱትን እየነገሩ በማረም መጓዝ ይጠበቅብናል፡፡

-----------
             “ዶ/ር አብይ የህዝብ አመፅ የወለዳቸው መሪ ናቸው”
                 ዶ/ር ንጋት አስፋው (ፖለቲከኛና የዩኒቨርሲቲ መምህር)

    ከኢህአዴግ የቆየ ባህሪ አንፃር የጠቅላይ ሚኒስትሩ ንግግር የተለየና ተስፋ ሰጪ ነው። አንደኛ ብሔራዊ እርቅ እንደሚፈፀም፣ ሁለተኛ ሀገርን የማረጋጋት ሥራ እንደሚሰራ መናገራቸው መልካም ነገር ነው፡፡ ኢትዮጵያዊ አንድነትን ማጠናከር ላይ ያደረጉትም ንግግር፣ ከዚህ ቀደም ከምናውቀው የድርጅቱ  ባህሪ የተለየ ነው፡፡ ይህቺ ሃገር ከትውልድ ወደ ትውልድ በአንድነት ፀንታ መሸጋገር እንዳለባት ያቀረቡበት መንገድ፣ ለሁሉም ገዢ ሀሣብ ነው። በግል የጠቅላይ ሚኒስትሩ ንግግር የልብን ፍላጎትን የሚሞላ ቢሆንም ከኢህአዴግ የአብዮታዊ ዲሞክራሲ ባህሪና መርህ አንፃር፣ ቃላቸው ወደ ተግባር ይለወጣል የሚል እምነት የለኝም፡፡
ዶ/ር አብይ የህዝብ አመፅ የወለዳቸው፣ የማዕበሉ ውጤት ናቸው፡፡ ህዝባዊ አመፁ የፈጠራቸው መሪ እንጂ ከኢህአዴግ የፖለቲካ ባህል የተገኙ አይደሉም፡፡ ማዕበሉ ያመጣው፣ ያልታሰቡ መሪ ናቸው - ዶ/ር አብይ፡፡
በንግግራቸው ላይ የእስረኞች ጉዳይ አልተነሳም። ለኔ ይሄ ዋና ጉዳይ ነው፡፡ ስለ ፖለቲካና ዲሞክራሲ ያወሩበት ድምፀት ግን ጥሩ ነው፡፡ ለእርቀ ሰላም ጥሪ ማቅረባቸውም መልካም ነው፡፡ ነገር ግን በምን መንገድ? እንዴት የሚሉት አልተዳሰሱም። በንግግራቸው ልብን ከማሞቅ የዘለለ ህዝቡ ሲያነሳቸው የነበሩ ጥያቄዎች በሚገባ አልተነሱም። በኤርትራ ጉዳይ የያዙት አቋም ስንናፍቀው የነበረው ነው፡፡ ነገር ግን አሁን እውን ይሆናል ማለት አስቸጋሪ ነው፡፡ እኒህ አዲስ መሪ መጡ ማለት የሀገሪቱ ችግር ተፈታ ማለት አይደለም። ችግር መፈታት የሚጀምረው ፖለቲከኞች በነፃነት ሲወያዩ፣ አዳዲስ ሃሳቦች ሲፈልቁ ነው፡፡
እኔን ያስገረመኝ በ15 ዓመቱ ህውኃትን የተቀላቀለና በህውኃት የዲሞክራሲ ፀበል ተጠምቆ ያደገ ወጣት ሆኖ ሳለ፣ ስለ ኢትዮጵያዊነት ብዙዎችን ያስደመመ፣ ማራኪ ንግግር ማቅረቡ ነው፡፡ እኔ ጅማ ስሰራ፣ በግሌ ቤተሰቦቹንም እሱንም አውቀዋለሁ፡፡ ገጠራማ ከሆነ አካባቢ የወጣ ሰው ነው፡፡ ከንግግሩ ንቃተ ህሊናው የዳበረ መሆኑን ነው የተረዳሁት። ንግግሩም የራሱ እንደሆነ አያሻማም፡፡ ነገር ግን የሀገሪቱ ችግር የሚፈታው፣ ምርጫ ተደርጎ፣ በህዝብ የተመረጠ መሪ ሲመጣ ነው ብዬ አስባለሁ፡፡
በሌላ በኩል፤ ዶ/ር አብይ የወጣቱን ቀልብ የመያዝ አቅም አለው፡፡ ጊዜውንና ዕድሉን ከተጠቀመበት ጥሩ ነገር ሊፈጠር ይችላል፡፡ ዋናው ጊዜውን በአግባቡ መጠቀሙ ላይ ነው፡፡ የቂም በቀል ፖለቲካ ለአንዴና ለመጨረሻ ጊዜ ከሀገር ውስጥ ተነቅሎ መጥፋት አለበት ብዬ አምናለሁ፡፡  ይሄ ደግሞ እያንዳንዱን ኢትዮጵያዊ ይመለከታል፡፡   

--------

              “መሪዎች እንደ ፀሐይ በፈጣሪ የሚታዘዙ መሆን አለባቸው”
                  መጋቢ ሃዲስ እሸቱ አለማየሁ


    ጠቅላይ ሚኒስትሩ ባደረጉት ንግግር ደስ ብሎኛል፡፡ እንደ አንድ ኢትዮጵያዊ ተስፋ ሰንቄያለሁ። አስተማማኝ ደህንነት እፈልጋለሁ፤ ወጥቼ መግባት፣ ሃገሬ ውስጥ እንዳሻኝ መንቀሳቀስ እፈልጋለሁ፡፡ እሳቸው ያደረጓቸው ንግግሮች ለዚህ ማረጋገጫ ናቸው ብዬ አምናለሁ፡፡ በንግግራቸውም ደስተኛ ነኝ፡፡ እንዲህ ሃሳብና ንግግር እርሾ ናቸው፤ ተግባር ደግሞ ዱቄት ነው፡፡ እርሾና ዱቄት ተዋህዶ ደግሞ ዳቦ ይፈጠራል፡፡ በሃሳብና በንግግር እርሾነት፣ በተግባር ዱቄትነት መልካም ኑሮ የሚባለው ዳቦ ይጋገራል ብዬ ተስፋ አደርጋለሁ፡፡
ከጠ/ሚኒስትሩ ንግግር እኩል እኔን ያስደሰተኝ፣ በንግግራቸው የተደሰተው ህዝብ የነበረው ስሜት ነው፡፡ የኢትዮጵያ ህዝብ መሪው ምን አይነት ቋንቋ ይናገራል? የቱን እምነት ይከተላል? ከየት አካባቢ ነው የመጣው? የሚል ስሌት ውስጥ አይገባም፡፡ ህዝቡ የሚፈልገው በትክክል የሚመራውን ብቻ ነው፡፡ እኔ ለምሳሌ በምሳፈረው ታክሲ ውስጥ ያለው ሹፌር ፕሮቴስታንት ይሁን፣ ትግሬ ይሁን፣ አማራ ይሁን፣ ኦርቶዶክስ ይሁን፣ ሙስሊም ይሁን---- የማውቀው ነገር የለኝም፡፡ የኔ ፍላጎት መኪናውን በትክክል አሽከርክሮ ካሰብኩት ቦታ እንዲያደርሰኝ ብቻ ነው፡፡ ህዝባችን በትክክል የሚመራው፣ ትክክለኛ ሹፌር ካገኘ ጨዋ ተሳፋሪ ነው፡፡ ይሄን ልናይለት ይገባል፡፡
በሌላ በኩል በሃይማኖት አስተምህሮ፤ መሪዎች በፀሐይ ይመሰላሉ፡፡ ፀሐዩ ንጉሥ ይባሉ ነበር፤ ነገስታቱ፡፡ መሪዎች የፀሐይነት ባህሪ ሊኖራቸው ይገባል፡፡ በዓለም ላይ ፀሐይ ትልቁ የብርሃን ምንጭ ነው፡፡ ከዚያ ቀጥሎ ነው አምፖል፣ ጧፍ፣ ሻማ፣ ኩራዝ የሚመጣው፡፡ እነዚህ ደግሞ ሰው እየለኮ ሰው ራሱ ያጠፋቸዋል፡፡ ፀሐይ ግን በሰው ትዕዛዝ የምትወጣ የምትገባ አይደለችም፡፡ ስለዚህ መሪዎች እንደ አምፖል በቆጣሪ ሳይሆን እንደ ፀሐይ በፈጣሪ የሚታዘዙ መሆን አለባቸው፡፡ ሁለተኛ፤ ፀሐይ ከሰማይ በመለስ ለሁሉም ነው የሚያበራው፤ አምፖል ደግሞ ከጣራ በታች ለቤተሰብ ነው የሚያበራው፡፡ መሪዎች ፀሐይ ናቸው፡፡ ፀሐይን ለመሞቅ ኦሮሚኛም ሆነ ትግርኛ፣ እስልምናም ሆነ ክርስትና መመዘኛዎች አይደሉም፡፡ ሰው ሁሉ ይሞቃቸዋል፡፡ መሪዎችን ልክ እንደ ፀሐይዋ ሁላችንም እኩል የምንሞቃቸው፣ ሲያቃጥሉን ደግሞ እኩል አቃጥለውን እኩል የምንናገራቸው፣ ሲያጠፉ እኩል የምንወቅሳቸው፣ ሲያለሙ ደግሞ እኩል የምናመሰግናቸው እንዲሆኑ እንጠብቃለን፡፡
ኢትዮጵያውያን የፖለቲካ ሰዎችና የሃይማኖት ሰባኪዎችን የሚያመሳስሉን ሶስት ፀባዮች አሉ። አንደኛ እኛ የገባን ሁሉ ህዝቡ ገብቶታል ብሎ መደምደም፣ እኛ ያልገባን ሁሉ ህዝብ አልገባውም ብሎ መወሰን፣ በሌላ በኩል እኔ የወደድኩትን ሁሉ ህዝብ ይወደዋል፣ እኔ የጠላሁትን ሁሉ ህዝብ ይጠላዋል ብሎ ሚሊዮኖችን በአንድ ጫማ ውስጥ አስገብቶ ማቆም ወይም ደግሞ ጠቅልሎ በአንድ መስፋት ይታያል፡፡ ይሄ ችግር ነው፡፡ ከዚህ ችግር መውጣት ያስፈልጋል፡፡ አንድ ሰባኪ መፆም ካቃተው ምዕመኑን ማሳነፍ የለበትም። ፖለቲከኞችም እነሱ የወደዱትን ሁሉ ህዝቡ ይወደዋል ማለት አይደለም። እኛ የወደድነውን ህዝቡ የመውደድ ግዴታ የለበትም፤ ህዝቡ የወደደውን ግን የመውደድ ግዴታ አለብን፡፡
አዲሱ መሪያችን እነዚህን ሁሉ ዙሪያ መለስ አስተሳሰቦች አዋደው ይመሩናል የሚል ተስፋ አለኝ። በቀን ሦስት ጊዜ እንበላለን ብለን ስንጠብቅ፣ በቀን ሦስት ጊዜ ወደ መባላቱ ልናሽቆለቁል ነበር፤ ከዚህ የማምለጫ መንገዱን የጨበጥን ይመስላል፡፡
ከንግግሮቻቸው የማረከኝ አንድነትን የመነዘሩበት መንገድ ነው፡፡ እዚህ ሀገር ላይ ስለ አንድነት የተንሸዋረሩ አመለካከቶች አሉ። አንድነቱን የተወሰነ ሃይማኖት ወይም ብሄር አድርጎ የመረዳት ችግር አለ፡፡ እሳቸው መደመር ጥንካሬ፤ ብርታት ነው ብለዋል፡፡ በንግግራቸው የጠቀሷቸው የጦርነት ቦታዎች አሉ፤ እነዚያ ቦታዎች ላይ ደማችን ነው የፈሰሰው እንጂ ቋንቋችን አይደለም። የኢትዮጵያውያን ደም ነው የፈሰሰው፡፡ ስለዚህ አንድነትን የገለፁበት መንገድ ለኔ ጠንካራ ነው። ልዩነት መረገም አይደለም ብለዋል፡፡ ይሄ ሁሉም ሊቀበለው የሚገባ ሃሳብ ነው፡፡ የቋንቋና የህዝብ ብዛትን እንደ መርገም ሳይሆን እንደ በረከት መውሰድ ይገባናል፡፡ በሌላ በኩል እናታቸውን ያመሰገኑበት መንገድ አርአያነት ያለው ነው፡፡ ብዙ ባለስልጣኖች በአደባባይ ስለ ሃይማኖታቸው፣ ቤተሰባቸው፣ ሚስታቸው ሲናገሩ አንሰማም። እርግጥ ነው ስለ ሃይማኖታቸው እንዲናገሩ አንፈልግም፤ ምክንያቱም እኛ መሪ እንጂ ሼህ ወይም ፓትርያርክ አይደለም የሾምነው፡፡ እምነታቸውን ሳይሆን ሰውነታቸውን፣ በጎ ህሊናቸውን ነው የምንፈልገው፡፡

-----------
           “የጠ/ሚኒስትሩ ንግግር የብዙዎችን ስሜት የሚገዛ ነው”
                አቶ ግርማ ሰይፉ (የቀድሞ የፓርላማ አባል)

    የብዙዎችን ስሜት የሚገዛ በተሻለ ሁኔታ የተዘጋጀ ንግግር ነው ማለት ይቻላል - የጠቅላይ ሚኒስትሩ ንግግር፡፡ ዘወትር የምንሰማው አሰልቺ የሆነ፣ የካድሬ ቋንቋ የለበትም፡፡ ስለዚህ የካድሬ ንትርክ ላሰለቸን ሰዎች፣ እንዲህ አይነት ንግግርን ማድነቃችን ተገቢ ይመስለኛል፡፡
ከዚህ ውጪ ይዘቱን በተመለከተ፡- ኢትዮጵያ ውስጥ የነበሩ ችግሮችን በሙሉ በዚያ ንግግር ውስጥ ዘርዝሮ ለመግለፅ ቢሞከር፣ የፊደል ካስትሮ ንግግር ነው የሚሆነው፡፡ ጠ/ሚኒስትሩ ንግግራቸውን ማሳጠራቸው ተገቢ ነበር፡፡ ንግግራቸውን ለማሳጠር ሲሞክሩ፣ አንዳንድ ነገሮችን እኛ በፈለግነው ጥልቀት ላናገኛቸው እንችላለን፡፡ ይህም ሆኖ ጥሩ ጥሩ ነገሮች በንግግሩ ተነስተዋል። ከእነዚህ ውስጥ ይቅርታ የጠየቁበት መንገድ አንዱ ነው፡፡ በእርግጥ አቶ ኃይለማርያም “ይቅርታ” ማለትን አስለምደውን ነበር፡፡ ነገር ግን ይቅርታዎቹ ከልብ አይመስሉም ነበር፡፡ የዶ/ር አብይ ይቅርታ ከልባቸው መሆኑ ያስታውቃል። እያንዳንዱን ስማቸውን ጠርተው፣ ባለብን የዲሞክራሲ አያያዝ ችግር ምክንያት ህይወታቸውን ላጡ፣ በተለይ ቦርቀው ያልጨረሱ ህፃናት--- በማለት ይቅርታ መጠየቃቸው፣ ልባቸው ለተሰበረ ቤተሰቦች ትልቅ ትርጉም አለው፡፡ የእሳቸውንም ትልቅነት ያሳያል። ከዚያ በተጨማሪ የቀድሞውን ዘግተን አዲስ ምዕራፍ እንጀምር ተብሏል፡፡ ከዚህ በፊት ኢትዮጵያ ይህን ማድረግ የሚያስችል ብዙ አጋጣሚዎች አግኝታ አልተጠቀመችበትም፡፡ አሁን በዚያ ቁጭት ተነስተን፣ ይህን እንደ አንድ አጋጣሚ ተጠቅመን፣ ወደ ተሻለ ደረጃ ብንወስደው ጥሩ ውጤት ያመጣል የሚል እምነት አለኝ፡፡
ንግግሮቹን ወደ ተግባር ለመለወጥ፣ አንዳንዶቹ የፍቃደኝነት ጉዳይን የሚጠይቁ ናቸው፡፡ ኢትዮጵያውያን ዲሞክራሲ ያስፈልገናል ይገባናልም ነው ያሉት፡፡ ነፃነት ደግሞ ከመንግሥት የሚሰጥ ችሮታ አይደለም፤ ሰው በመሆናችን ብቻ ያገኘነው ነገር ነው ብለዋል - ጠ/ሚኒስትሩ፡፡ እስካሁን እንዲህ እውቅና መስጠት ነበር ችግር ሆኖ የቆየው። ሌላው የሃሳብ ልዩነትን ማክበር ነበር ትልቁ ችግር። አሁን ግን የሃሳብ ልዩነት እርግማን አይደለም ነው ያሉት፡፡ ስለዚህ የሃሳብ ልዩነት እርግማን ካልሆነና እንዲያውም በረከት ከሆነ፣ ዲሞክራሲንና ነፃነትን ማፈን አያስፈልግም፤ ምክንያቱም አፈና የሚኖረው ሌላውን ለመስማት ፍላጎት ሳይኖር ሲቀር  ነው፡፡
ለእናታቸው ያቀረቡትን ምስጋና ስሰማ እንባዬ መጥቷል፡፡ ለማርች 8 ለእናቴ የፃፍኩት አንድ ግጥም ነበረ፡፡ እሱን ነው ያስታወሰኝ፤ ንግግራቸውን ብቻዬን ስሰማው ነበርና እንባዬ ነው የመጣው። እናቱን የሚወድ፣ ለቤተሰቦቹ ዋጋ ያለው ሰው፣ ልጅ የሞተባትን እናት ቁስልና የህሊና ጠባሳ ይረዳል። ይሄን በማለታቸው በእውነት ጥሩ ነገር ነው ያደረጉት፡፡
እግዚአብሔርን የሚፈራ ሰው፣ መብራት አጥፍቶ ግፍ አይሰራም፡፡ ምክንያቱም ሰው ባያየኝ፣ የሚያየኝ ፈጣሪ አለ ይላል፡፡ አቶ ኃይለማሪያም አማኝ በመሆናቸው፣ ፈሪሃ እግዚአብሔር ነበራቸው፡፡
 ሌላው ኢትዮጵያ ለዘለዓለም ትኑር፤ ፈጣሪ ኢትዮጵያን ይባርክ ሲሉ በጣም ነው ደስ ያለኝ። እኔ በፓርላማው እሳቸው ያሉትን ቃል በቃል በተናገርኩ ጊዜ፣ ፓርላማው በሙሉ ነበር  የሳቀው፡፡ ዛሬ ግን አጨብጭበዋል፡፡ የፓርላማው አባላት ለዶ/ር አብይ ሲያጨበጭቡ፣ ያኔ ያደረግሁት ነገር የበለጠ ትክክል እንደነበረ ተጨማሪ ማረጋገጫ አግኝቻለሁ፡፡

----------
                   “ህዝቡ ለጠቅላይ ሚኒስትሩ ጊዜ ሊሰጣቸው ይገባል”
                     አያልነህ ሙላት (ገጣሚና ጸሃፌ ተውኔት)

    በከፍተኛ ስሜት ነው ንግግሩን የተከታተልኩት። ይህ የሆነበት ምክንያትም ለብዙ ዘመናት ከኢትዮጵያ ምድር ደብዛቸው ጠፍቶ የነበረ ኢትዮጵያዊነትና አንድነት የሚሉት ጉዳዮች ጎልተው በመውጣታቸው  ነው፡፡ ይህ ለኔ ከፍተኛ ስሜትን ነው የፈጠረብኝ፡፡ በአብዛኛው የተጠማነው ይሄን ነገር ነበር፡፡ የጠ/ሚኒስትሩ ንግግር ይሄን ጥማት አርክቶልናል፡፡ ግን በንግግር ብቻ መርካት አስቸጋሪ ነው፡፡ ንግግሩ እንዴት በተግባር ይተረጎማል? የሚለው የኢትዮጵያ ህዝብ ለወደፊት በተስፋ የሚጠብቀው ይመስለኛል፡፡ ንግግሩ ወደ ተጨባጭ ነገር ተቀይሮ ለውጥ መምጣት አለበት፡፡ አለበለዚያ በቃላት መካካብ ብቻ ሆኖ ይቀራል የሚል ስጋት ስላለኝ፣ በቶሎ ወደ ተግባር መለወጥ ይገባዋል፡፡
ይህን ለማድረግ በዋናነት ሦስት ነገሮች የሚያስፈልጉ ይመስለኛል፡፡ አንደኛው፤ ኢህአዴግ ንግግሮችን የህዝብን ቁጣ ለማብረድ ብቻ የተጠቀመበት ሳይሆን ከልቡ አምኖ የፈፀማቸው መሆናቸውን ማረጋገጥ አለበት፡፡ ሁለተኛው፤ አዲሱ ጠቅላይ ሚኒስቴር ይሄን ሳያረጋግጡ ወደዚህ ስልጣን ይሸጋገራሉ ብዬ አላምንም፡፡ ምክንያቱም ከጀርባቸው ያኮረፈ ትውልድ አለ፣ በጥቅም የተሳሰረና የበለፀገ ካድሬ አለ፡፡ ይሄን እንዴት ወደ ለውጡ ማምጣት እንደሚቻል ማሰብ ያስፈልጋል፡፡
ይሄ ተሃድሶ /ለውጥ/ ስለሆነና በማሳመንም ብቻ የሚከወን ስላልሆነ ጠ/ሚኒስትሩ በቀላሉ ይወጡታል ብዬ አልገምትም፡፡ ህዝቡም ይሄን ነገር አሁኑኑ ውለዳት ከማለት ይልቅ ጊዜ ሊሰጣቸው ይገባል፡፡ ትዕግስት ከሌለ ጠቅላይ ሚኒስትሩን ራሳቸውን ወደ ተስፋ መቁረጥ ስለሚመራቸው ውጤቱ ጥሩ አይሆንም፡፡ ህዝቡ ጠቅላይ ሚኒስትሩን እንደ ጋን የሚቆጥራቸው ከሆነ ጠጠር ሆኖ ሊደግፋቸው ይገባል፡፡ ምሁሩም ከትዝብት ወደ ተሳትፎ መሻገር አለበት፡፡
እኚህ ጠቅላይ ሚኒስትር በንግግራቸው ይቅርታ መጠየቃቸው ትልቅ ትምህርት ነው፡፡ እርግጥ ነው አሁን የፓርቲ ለውጥ አልተደረገም፡፡ ነገ የምንጠብቀው ደግሞ ያለ ጥይት ድምፅ፣ አንድ ፓርቲ በአንድ ፓርቲ ሲለወጥ ማየት ነው፡፡ በቀጣይ በጉጉት የምንጠብቀው ይሄንን ነው፡፡
ተፅፎ የተሰጠውን የማያነብ መሪ ነው ያገኘነው። ለዚህም ወላጅ እናታቸውን ማመስገናቸው፣ ከዚህ በፊት የሰለቹ ቃላትን አለመጠቀማቸውና ስለ ሀገራቸው ያላቸውን ምኞት መግለፃቸው ንግግሩ የራሳቸው መሆኑን አመላካች ነው፡፡ ዶ/ር አብይ እናታቸውን ሲያመሰግኑ፣ ሃገራቸውን እንዳመሰገኑ ነው የገባኝ፡፡ ሚስታቸውን ሲያመሰግኑ የስኬታቸውን ምንጭ ነው ያመሰገኑት፡፡ ይሄ አስደሳች ነው፡፡ እኔ በንግግራቸው በጣም ነው ደስ ያለኝ፡፡

“ሁሉም ነገር ይለወጣል፡- ከለውጥ ህግ በስተቀር”
ከዕለታት አንድ ቀን የፋሲካ እለት እናት፣ አባት፣ እንግዳና ልጅ ለመፈሰክ እየተዘጋጁ ነው፡፡ ልጁ እንግዳ ኖረም አልኖረም ከሰው ፊት እያነሳ የመብላት ልማድ አለው፡፡
እናትና አባት ተሳቀዋል! እንግዳ ስለ ልጁ ጠባይ አያውቅም፡፡ እናትና አባት ልጁን ቆጥ ላይ አውጥተው አሠሩት፡፡
ልጅ ማልቀስ ጀመረ!
እንግዳው ግራ ገባውና፤
“ምን አርጎ ነው ይህንን ልጅ ያሠራችሁት?” ሲል ጠየቀ፡፡
አባት፤
“አመል አለበት፤ ከሰው ፊት እያነሳ ስለሚበላ በልተን እስክንጨርስ ቢታሠር ይሻላል ብለን ነው”
እንግዳው፤ በሀፍረት፤
“ይሄ በዕውነቱ የማይገባ ነገር ነው፡፡ ነውር ነው! በሉ ፍቱትና መጥቶ አብሮን ይብላ፡፡ ልጅ‘ኮ ነው ምን ያውቃል?”
ባልና ሚስት የምንተ-እፍረታቸውን ልጁን ፈቱትና ገበታው ዘንድ እንዲቀርብ ተደረገ፡፡
ዶሮ ወጡ መጣ፡፡
ለባል ፈረሰኛ ወጣ፡፡
ለእንግዳ እግር ተሰጠ፡፡
ለሚስት መላላጫ ወጣለት፡፡
ለልጅ ዕንቁላል ቀረበለት፡፡
ወጡ ወጣና መቀመስ ተጀመረ፡፡
ይሄኔ ልጅ የእንግዳውን የዶሮ-እግር ላፍ አደረገ፡፡
አባት፤ “እንዴ ይሄ ባለጌ!”
እናት፤ “ይሄ አሳዳጊ የበደለው ልጅ!” አለች እናት
ልጁ ሌላ ቤት ያደገ ይመስላል፡፡ ሌላ እግር ለእንግዳው ወጣለት፡፡
ልጅ ከትንሽ ሰኮንድ በኋላ አሁንም የዶሮዋን ሥጋ ላፍ አደረጋት፡፡
እናት- “ኧረ ይሄ አሳዳጊ የበደለው ልጅ ምን ቢደረግ ይሻላል?”
አባት “ማጋጨት ነው የሚሻለው!” ብለው ብድግ አሉ፡፡
እንግዳው፤ “ኧረ ልጅ ነው ተውት፡፡ የኛ ልጆችኮ ድስቱን ራሱን ይዘው ነው የሚሮጡት።
አባት፤ ኮራ ብለው፡-
“አይ፤ ለሱስ ደህና አርገን ቀጥተነዋል!”
* * *
አስተዳደግ ከቤት ይጀመራል፡፡ ት/ቤት ይከተላል፡፡ ህብረተሰብ ይቀበለዋል፡፡ በዚህ ሶስት ማዕዘን ውስጥ ነው ትውልድ የሚቀረፀው፡፡ በሥነ-ስርዓት የተቀረፀ ወጣት ለወግ-ማዕረግ ይበቃል፡፡ አድጎ ተመንደጎ መልካም ዜጋ የመሆን ዕድሉ ሰፊ ነው፡፡ መልካም ወጣቶች ተረካቢ ትውልድ የመሆን ኃላፊነታቸው ለመወጣት ዝግጁ ይሆናሉ፡፡ ተስፋቸው ብርሃናማ ይሆናል፡፡ ከሁሉም በላይ ደግሞ ለአደራ መብቃትን የመሰለ ነገር የለም፡፡ አንድ ገጣሚ እንዳለው፡-
“መፅሀፍ አንብቤ እፎይ ባልኩኝ ሰዓት
ምነው ዛፍ በሆንኩኝ እያልኩ እመኛለሁ   
ወይ ፍሬ አፈራለሁ
ወይ ጥላ እሆናለሁ
ቢያንስ አንዲት ወፍ በግል አምናኝ ተቀብላኝ
ጎጆ ቤትዋን ፈቅዳ እንደምትለግሠኝ፤ እተማመናለሁ፡፡
ያኔ በትክክል ለአደራ እበቃለሁ!” ማለት አግባብ ነው፡፡ እንደዚህ ያለ ሀሳብ ያለው መሪ ማግኘት መታደል ነው፡፡
ብዙ ቃል ተገብቶልን ላልተሳካልን ህዝቦች፤ ዛሬም ቃል ብርቃችን ነው፡፡ “ጊዜ የሥልጣን እጅ ነው!” እንዳለው ፀጋዬ ገ/መድህን፤ ጊዜን መጠበቅ በጎ ነው! ጊዜ የተግባር ፈተና ነውና! በሀገራችን በኢትዮጵያ አያሌ ያመለጡ ዕድሎች ነበሩ፡፡ በ1966 እና በ1983። ዛሬ ሌላኛው ዕድል የተከሰተ ይመስለናል፡፡ እንደገጠመኝ ሳይሆን እንደ ሂደት አስበን አጋጣሚውን መጠቀም ይጠበቅብናል! መሪዎች ምን ያደርጉልናል ከማለት ባሻገር እኛ በሀገራዊ ግዴታችን እንደዜጋ፣ እንደ ቡድን፣ እንደ ተቋም … ምን ዓይነት አዎንታዊ ሚና እንዲኖረን እናድርግ? እንበል፡፡ መሪዎችን ህዝቦች ሊቀርጿቸው እንደሚችሉ አንዘንጋ! ሁኔታዊ አስተዋፅዖዎች አያሌ ናቸው፡፡ ግብዓቶችን ፈልፍለን እንወቅ፡፡ ጊዜን በአግባቡ፣ እንጠቀምበት፡፡ የመደማመጥ ባህላችንን እናስፋ፡፡ ሥርዓትን በአግባቡ ለመለወጥ ተቋማዊ አቅም እንገንባ፡፡ ዲሞክራሲን በልካችን እንስፋ!
“ሁሉም ነገር ይለወጣል-ከለውጥ ህግ በስተቀር!” ለውጥን መውደድ እንጂ መፍራት አያስፈልግም፡፡ ትዕግሥትና ሆደ ሰፊነትን ማስፋት እንጂ “ትዕግሥት ፍርሃት አይደለም” እያሉ መፎከር አይበጅም፣
በጥንቃቄና በብልህነት አገርን ማደራጀት፣ በዙሪያችን ያሉ ወዳጆችን በሚገባ ማቀፍና የልዩነት ባለቤቶችን ማክበር፣ በቀና ልቦና ማነጋገር ወሳኝ ነው! አማካሪዎች የሥራ-ቦታ መፍጠሪያ አካላት መሆን የለባቸውም! በአገር- መውደድና ወገባቸውን ጠብቅ አድርገው የሚያሰሩ ሊሆን ይገባል! መልካም አማካሪዎችን ማግኘት ሰማኒያ በመቶ ሥራን ማገባደድ ነው! ለሀሳብ አክብሮትና ዋጋ መስጠት፣ ለትክክለኛ ግምትና ለሁነኛ ዕቅድ መሠረት የመጣል ያህል ነው! ከሁሉም በላይ፤ “መካር የሌለው ንጉሥ፣ ያለ አንድ ዓመት አይነግሥ” የሚለውን አንርሳ!

Saturday, 14 April 2018 15:04

 በወሊድ ጊዜ የመድማት ሁኔታ ሲያጋጥም የህክምና እርዳታ ካልተደረገ በህይወት መቆየት የሚቻለው ለሁለት ሰአታት ብቻ ነው፡፡  
‹‹የመጀመሪያ ልጄን ነው አሁን የወለድኩት፡፡ ክትትሉን ስጀምር ግን የኤች አይቪ ቫይረስ በደምሽ ውስጥ አለ ስባል በመጀመሪያ በጣም ነበር የደነገጥኩት። አዝኛለሁም። በዚህ ላይ እርጉዝ ነበርኩ፡፡ ምን ማድረግ አለብኝ ብዬ ስጨነቅ ከቆየሁ በሁዋላ ሐኪሞቹ ባለቤትሽን ጥሪው ብለው ወረቀት ሰጡኝ፡፡ እሱም ያረገዝሽው አንቺ ነሽ እንጂ እኔ አይደለሁም፡፡ ለምን እሄዳለሁ ብሎ  በጣም ተቆጣ፡፡ ከብዙ ማግባባት በሁዋላ ሲሄድ እሱ ከቫይረሱ ነጻ መሆኑ ተነገረው፡፡ እኔ ይህን ስሰማ በጣም ተደሰትኩኝ። እሱ ግን በተገላቢጦሽ በጣም አዘነ፡፡ ሐኪሞቹ ግን ሁለታችንንም በጣም አረጋግተው እንድንግባባ አደረጉን፡፡ እንዴት ኑሮአችንንም መቀጠል እንዳለብን አስረዱን፡፡ አሁን በዚያ መመሪያ መሰረት ልጃችንም የእርግዝና ጊዜውን ጨርሶ ይሄው ተወልዶአል፡፡ በአሰላ ሆስፒታል ያሉ ሐኪሞችን እጅግ በጣም እናመሰግናለን፡፡ ሕይወታችንን ካለምንም ጭንቀት እንድንቀጥል ረድተውናል፡፡››
በአሰላ ሆስፒታል ወላዶች ክፍል ያገኘናት ወላድ፡፡  
በአሰላ ሪፈራል ሆስፒታል ያገኘናት ታካሚ ይህች ብቻ አይደለችም፡፡ በሆስፒታሉ ተዘዋውረን እንደተመለከትነው ሌሎችም ታካሚ እናቶች በሆስፒታሉ ለሚሰሩ አዋላጅ ነርሶች ለሚሰጡት ክብር፤ ፍቅርና ከበሬታ ያለው ሙያዊ አገልግሎት ምስክርነት በመስጠት በእጅጉ አመስግነዋል፡፡
የማዋለጃ ክፍል ኃላፊ የሆኑት ሲ/ር ማሽላ አዲሴ በአዋላጅ ነርስነት ለ18 አመታት ሰርተዋል፡፡ እሳቸው እንደገለጹት ሙያቸውን በጣም ያከብሩታል፡፡ይወዱታልም፡፡ እናቶችን በሰላም ማዋለድ ማለት ሕይወት እንድትቀጥል ማስቻል ማለት ነው፡፡ አንዲት እናት በወሊድ ወቅት ተጎዳች ማለት ደግሞ በተቃራኒው ሕይወት እንዲቋረጥ ማድረግ ነው፡፡ ከዚህ በላይ የሚያስደስትም ሆነ የሚያሳዝን አጋጣሚ የለም እንደ አዋላጅ ነርስ ማሽላ አባባል፡፡
የአሰላ ሆስፒታል በአርሲ ዞን ሪፈራል ሆስፒታል ነው፡፡ ስለዚህም እናቶች ከዲስትሪክት ሆስፒታል ፣ከጤና ጣቢያዎች በሪፈራል ለህክምና ይመጣሉ፡፡ ከዚህም በተጨማሪ ከአርሲ ዞን ዙሪያ ከከተሞችም ይሁን ገጠሮች አካባቢ በቀጥታ አሰላ ሆስፒታል ብለው የሚመጡ እናቶችም በርካታ ናቸው፡፡ አንዲት እናት የሆስፒታሉን አገልግሎት ፈቅዳ ከመጣች ተገቢውን አገልግሎት ታገኛለች፡፡
ከየጤና ተቋማቱ በሪፈር የሚመጡ ታካሚዎች ጉዳያቸው ይለያያል፡፡ ከሆስፒታሎች የሚመ ጡት እናቶች የኦፕራሲዮን አገልግሎት የማይሰጥባቸው አጋጣሚዎች ሲኖሩ… ለምሳሌም መብራት ሳይኖር… የጄኔሬተር ብልሽት ሲያጋጥም በአፋጣኝ ወደ አሰላ ሆስፒታል ይመጣሉ። ዲስትሪክት ሆስፒታሎች የደም አቅርቦት ከሌላቸው በተለይም ከወሊድ በሁዋላ የደም መፍሰስ ሲያጋጥም እናቶችን በአስቸኩዋይ ወደ አሰላ ሆስፒታል ይልካሉ። ጤና ጣቢያ ዎች ደግሞ አንዲት እናት የምጥ መራዘም ሲገጥማት ወይንም ከእርግዝና ጋር በተያያዘ የደም ግፊት (ፕሪክላምፕስያ ኢክላምፕሲያ) ሲያጋጥም ወደሆስፒታሉ ይልኩዋታል፡፡ ከዚህ ውጪ ደግሞ ብዙዎች አሰላ ሪፈራል ሆስፒታል ነው ከሚል ማንም ሪፈር ሳይላቸው ወደ ሆስፒታሉ ይመጣሉ፡፡ የማዋለጃ ክፍሉ የኦፕራሲዮን ክፍሉን ጨምሮ ያለው 37/ ሰላሳ ሰባት አልጋ ብቻ ነው። ስለዚህም ሪፈር ሳይባሉ ወደሆስፒታሉ የሚመጡት ማለትም ጤነኛ የሆኑ ትና በጤና ጣቢያ መውለድ የሚችሉት እናቶች የጤና ቸግር ገጥሞአቸው ለሚመጡት እናቶች የአልጋ መጣበብ እንዲኖር ያደርጋሉ፡፡ ስለዚህም ታካሚዎችን አንዱን ካንዱ ጋር እያስተያየን እያሸጋ ሽገን እንዲሁም አልጋ ከሌሎች ክፍሎች በመዋስ ጭምር ወላዶችን በኮሪደር ላይ ሳይቀር  በማስተኛት አገልግሎትን እንሰጣለን፡፡
የአሰላ ሪፈራል ሆስፒታል በአንድ ወር እስከ 550/አምስት መቶ ሀምሳ ወላዶችን ያዋልዳል፡፡ ወደሆስፒታሉ ከሚመጡት ወላዶች ውስጥ አብዛኞቹ በሰላም ተገላግለው ወደቤተሰባቸው የሚቀላቀሉ ሲሆን አንዳንድ ጊዜ ግን ችግር መፈጠሩ አይቀርም፡፡ ለምሳሌም በጤና ጣቢያ ቆይተው የተለያዩ የጤና ችግሮች ገጥመዋቸው ለሞት ሊዳረጉ የደረሱ እናቶች ሲላኩ እነሱን ለማትረፍ እጅግ ከፍተኛ ዋጋ የሚያስከፍል ሁኔታ ያጋጥማል፡፡ በ2007 እና 2008 ዓ.ም በሆስፒታሉ ያጋጠመ የእናቶች ሞት በርከት ያለ የነበረ ሲሆን በ2009/ዓም ግን 6480/እና ቶች የወለዱ ሲሆን በአንድ አመት ውስጥ 7/ሰባት እናቶች ሞተዋል፡፡ ከእነዚህም አብዛኞቾ በሪፈራል መጥተው ገና ከሆስፒታሉ ግቢ ሲደርሱ ወይንም መንገድ ላይ ሞተው የደረሱ ናቸው። እነዚህ እናቶች ለሞት ምክንያት የሆናቸውም በወሊድ ጊዜ የደም መፍሰስ፤ የደም ግፊት፤ የደም መርጋት ናቸው፡፡ አንዲት እናት ስትሞት ሆስፒታሉ የማጣራት ስራ ይሰራል፡፡ ለምን ሞተች፤ የትጋነው ችግሩ የተፈጠረው የሚለውን ሪፈር ካደረጉት ጤና ጣቢያዎችና እናትየው ከመጣ ችበት መንደር መረጃ በመሰብሰብ ስህተቱ እንዳይደገም ለማድረግ ጥረት ይደረጋል፡፡ በእርግጥ በአብዛኛው ከቤታቸው ሳይወጡ የተፈጠረ መዘግየት ሲሆን ሌላው ደግሞ ከደረሱበት ሆስፒታል ወይንም ጤና ተቋም በፍጥነት ሪፈር አለመደረግ፤ በበአምቡላንስ ተጉዋ ጉዘው ከሆስፒታል እስኪደርሱ በሚኖረው መዘግየት እንደህመሙ ሁኔታ እናቶች ሊጎዱ ይችላሉ፡፡ በወሊድ ጊዜ የመድማት ሁኔታሲያጋጥም በህይወት መቆየት የሚቻለው ለሁለት ሰአታት ብቻ ነው፡፡ የደም ግፊትም እርዳታ በፍጥነት ካላገኘ እንደዚሁ በትንሽ ጊዜ ሊገድል ይችላል፡፡
ሲስተር ማሽላ እንዳሉት የእናቶችን ሕይወት በማትረፍ በኩል ሁልጊዜም ደግመን ደግመን የምንነ ጋገረውና ነገር ግን ዛሬም የሚያጋጥመው ችግር መዘግየት ነው፡፡ በመጀመሪያ ደረጃ ህብረተሰቡ ሊረዳው የሚገባው ነገር አንዲት እርጉዝ ሴት የመውለጃ ጊዜዋ ሲቃረብ ቅድመ ጥንቃቄ ማድረግ እንደሚገባው ነው፡፡ መጉዋጉዋዣው፤ ገንዘቡ፤ ወደጤና ተቋሙ የማድረስ ኃላፊነት፤ የመሳሰሉትን ሁሉ ቀድሞ በማሰብ ምጥ በሚጀምርበት ጊዜ በፍጥነት በአቅራቢያ ወደሚገኘው ጤና ተቋም ማድረስ ተገቢ ይሆናል፡፡ እናቶች በምጥ በሚያዙበት ጊዜም ይሁን በክትትል ወቅት በቀረቡበት ጤና ተቋም ሊያገኙት ከሚችሉት እርዳታ በላይ የሆነ ችግር ሲገጥማቸው በፍጥነት ወደሚቀጥለው ደረጃ ማስተላለፍ ሙያዊ ግዴታ ነው፡፡ አንዳንድ ጊዜ ግን እናትየው ከሞት አፋፍ ስትደርስ ሪፈር ብትደረግም ሊያጋጥም ከሚችለው አደጋ ለማዳን ከማይቻልበት ደረጃ ሊያደርስ እንደሚችል መገመት ይገባል፡፡ በእርግጥ ይህ ሁኔታ በመሻሻል ላይ መሆኑ ባይካድም አሁንም ይህቺ እናት አትተርፍም እየተባሉ እየመጡ በብዙ መስዋእ ትነትና ትግል የተረፉ ብዙዎች ናቸው፡፡ ስለሆነም በ2010 ዓ/ም የእናቶች ሞት እስከአሁን አላጋጠመንም፡፡
‹‹…እኔ ጫልቱ እባላለሁ፡፡ የምኖረውም በዚሁ በአሰላ ከተማ ነው፡፡ አሁን እርግዝናዬ ዘጠኝ ወር ሆኖታል፡፡ ነገር ግን በሆስፒታሉ አልጋ ይዤ ከተኛሁ ሁለት ወር ሆኖኛል። ወደሆስፒታል መጀመሪያ የመጣሁት የደም መፍሰስ አጋጥሞኝ ነው፡፡ እኔ ባለሙያ ዎቹን በጣም ላመሰግን እወዳለሁ፡፡ ምክንያቱም ሁልግዜ ቀንና ማታ ወይንም የበአል ቀን ሳይባል በጠራናቸው ወይንም በፈለግናቸው ጊዜ ካጠገባችን ናቸው፡፡ እናቶች እንደዚህ ያለ እንክብካቤ የሚየገኙ ከሆነ አይሞቱም ማለት ነው፡፡››
የመውለጃዋ ቀን እስኪደርስ በማዋለጃው ተኝታ የምትጠባበቅ እናት ምስክርነት…
ሲ/ር ማሽላ እንዳሉት ከላይ ሃሳብ የሰጠችው እናት በሆስፒታል የተኛችው እንግዴ ልጅዋ ከልጅዋ ስለቀደመና የደም መፍሰስ ስላጋጠማት ነው፡፡ ይህች ሴት ወደመጸዳጃ ለመሄድ ወይንም ለአንድ አፍታ ሰው ለማናገር ካልሆነ በስተቀር ከአልጋ እንድትወርድ አይፈቀድላትም፡፡ ሆስፒታሉ በእርግጥ የእናቶች ማቆያ የለውም፡፡ ነገር ግን እንደችግሩ ሁኔታ በቅርብ ሐኪም ሊከታተላቸው የሚገባ ሲሆን የመውለጃ ቀናቸው እስኪደርስ ድረስ በሆስፒታሉ እንዲቆዩ የሚደረግበት አሰራር ግን አለ፡፡ ለዚሁ አሰራር እንዲያመች ምክንያት ያላቸው እናቶች የሚተኙበት ተብሎ ሁለት ክፍል ተለይቶአል፡፡ በዚህ ክፍል ውስጥ ሁለት ወርም ሆነ ሶስት ወር ድረስ ተኝተው ሁኔታውን የሚከታተሉበት አሰራር አለ፡፡ ለወደፊቱ ግን ሆስፒታሉ አዲስ ፎቅ እያሰራ ስለሆነ ያንጊዜ እናቶች የሚቆዩበት የእናቶች መቆያ ቤት ይኖራል፡፡
ከኤችአይቪ ጋር በተያያዘ የሚሰጠው አገልግሎት ወደርና ገደብ የሌለው ነው ማለት ይቻላል፡፡ ማናኛዋም እናት በቀጥታም ትምጣ ወይንም በሪፈር …ከኤችአይቪ ጋር በተያያዘ ሙሉ የምክር አገልግሎትና አስፈላጊው ምርመራ ይካሄዳል፡፡ ለምስክርነት ቀድሞ የነበረውን ሁኔታ እና የአሁኑን ለማስተያየት ቢሞከር ልዩነቱ እጅግ በጣም ሰፊ ነው፡፡ ከተወሰኑ አመታት ወዲህ መንግስት በሰጠው ልዩ ትኩረት የተነሳም በጣም የሚያስደስትና የሚያኮራ ሁኔታ አለ፡፡ ቫይረሱ በደማቸው ላለ እናቶችና ልጆቹ ሲወለዱ ከሚደረገው የህክምና ጥንቃቄ በተጨማሪ ቫይረሱ በደማቸው ያለ እናቶች በሚያደርጉት የእርስ በእርስ ውይይት የተነሳ በአሰላ ሆስፒታል 99.9% የሚሆኑት ሕጻናት ከቫይረሱ ነጻ ሆነው ተወልደዋል ብለዋል ሲ/ር ማሽላ አዲሴ የአሰላ ሆስፒታል ማዋለጃ ክፍል ኃላፊ፡፡

  ‹‹…እኔ ትዳር በያዝኩ በሶስተኛው አመት የመጀመሪያ ልጄን አረገዝኩ፡፡ ከዚያም በአቅራቢያዬ ወደሚገኝ ሆስፒታል ሄድኩና ምርመራ መጀመር እንደምፈልግ ነገርኩዋቸው። እነርሱም ተቀብለውኝ ምርመራውን ስጀምር ባለቤቴን እንድጠራ ተነገረኝ፡፡ ለምንድነው? ብዬ ብጠይቅ መጀመሪያ ሁለታችሁም ደም ብትሰጡና ብትታዩ ጥሩ ነው፡፡ ተባልኩኝ፡፡ ከዚያም ወደቤት ተመልሼ የተባልኩትን ነገርኩና የተሰጠንን የጥሪ ወረቀት ስሰጠው…በድንገት ብድግ ብሎ በጥፊ መታኝ፡፡ ምንሆነህ ነው? ብዬ ስጠይቀው በወደቅሁበት በእርግጫ ደገመኝ፡፡ እንደምንም ተጥመልምዬ ከወደቅሁበት ተነሳሁኝ፡፡ እዛው ሄደሽ ጣጣሽን ጨርሺ፡፡ እኔ የምጠራበት ምን ምክንያት አለ? የሆንሽውን እዛው አያክሙሽም? እኔ ለምን እፈለጋለሁ? ብሎ ጮኸብኝ፡፡ ስንጯጯህ የሰሙ ሰዎች ገብተው ገላገሉንና በቀጣዩ ቀን ወደሆስፒታል አብረን ሄድን፡፡ ምርመራውንም የግድ አደረገ፡፡ ነገር ግን ሁለታችንም ቫይረሱ በደማችን ውስጥ የለብንም፡፡ እኔ ግን በዚያ ዱላ ምክንያት ታምሜ ጽንሱ ተቋረጠ፡፡ ጽንሱም ብቻ ሳይሆን ኑሮአችንም ፈረሰ፡፡ ምክንያቱም ቫይረሱ በደማችን ውስጥ ቢገኝ ኖሮ እንደሚገለኝ ከዚያው ከሆስፒታል ነግሮኝ ስለነበር ነው፡፡ እንደዚህ ያሉ ሰዎች አርቆ ማሰብ የተሳናቸውና በዘመኑ የሌሉ ሁዋላቀሮች ስለሆኑ ቢመከሩ ጥሩ ነው፡፡…››
ከላይ ያነበባችሁት ታሪክ በአምቦ ከተማ ቡና እያፈላች የምትተዳደር ወጣት ምስክርነት ነው፡፡ በአምቦ አጠቃላይ ሆስፒታል የማዋለጃ ክፍሉን የስራ እንቅስቃሴ ለመመልከት በስፍራው በተገኘንበት ጊዜ ጠበብ ባለ ቦታ ታካሚና አሳካሚ የሆኑ ሰዎች ሲጨናነቁ ተመልክተናል፡፡  ሁኔታውን ለመመልከት ዘልቀን መግባት ነበረብን፡፡ የነበረውን ሁኔታ እንዲያብራሩልን የህክምና ባለሙያዎችን አነጋግረናል፡፡ በቅድሚያ ያገኘናቸው በሱፈቃድ ባልቻ በአምቦ አጠቃላይ ሆስፒታል አዋላጅ ነርስ ናቸው፡፡
ጥ/    በሆስፒታሉ ለመታከም የሚመጡ ተገልጋዮች ከየት ከየት ናቸው?
መ/    በአምቦ ሆስፒታል የሚታከሙት የጽንስና ማህጸን ታካሚዎች የሚመጡት በአጠቃላይ በምእራብ ሸዋ ካሉት ወረዳዎች ካሉ ጤና ጣቢያዎችም ሆነ ሌሎች የህክምና ተቋማት ሲሆን ስፍራዎቹም ጉደር፤ ሸነን፤ ከሚባሉት እና በአብዛኛውም በግላቸው የሚመጡ ናቸው። በአብዛ ኛው የሚመጡት እናቶች ሕመምም በድንገት ጽንስ መቋረጥና እንዲሁም በተለያዩ ችግሮች ምክንያት ሕጉ በሚፈቅደው መሰረት ፈቅደው ጽንስ ለማቋረጥ የሚመጡም አሉ። ሆስፒታሉ በሪፈር ሕመምተኞችን የሚቀበልባቸው ተብሎ የተመደቡለት ጤና ጣቢያዎች ቢኖሩም በድንገተኛ የሚመጡት ግን ከየትኛውም አካበቢ  ወይንም በግላቸውም ቢሆን አይመለ ሱም፡፡ ምናልባት ሕክምናው የሚሰጥበት ስፍራ ቢጠብና ቢጨናነቅ እንኩዋን ሕይወትን ሳናተ ርፍ ወደሌላ ቦታ እንዲሄዱ አናደርግም፡፡ በእርግጥ ከአሁን ቀደም ሁሉ ነገር በዚሁ ሆስፒታል ብቻ ተጨናንቆ የሚሰጥ ሲሆን አሁን ግን ሌላ የሪፈራል ሆስፒታል ስለተከፈተ ከአቅም በላይ የሆኑትን ወደዚያ እንልካለን፡፡      
በመቀጠል ያነጋገርነው ማትያስ ለሜሳ አዋላጅ ነርስ የማዋለጃ ክፍሉ ኃላፊ ናቸው፡፡
ጥ/    የማዋለጃ ክፍሉ አቅም ምን ይመስላል?
መ/    ማዋለጃ ክፍሉ በጣም የሚጨናነቅ ጠባብ እና ውስን አልጋዎች ያሉት ነው፡፡ በእርግጥ የአምቦ ዩኒቨርስቲ ሪፈራል ሆስፒታል ከመጀመሩ በፊት እጅግ በጣም የሚጨናነቅ ነበር፡፡ በአሁኑ ወቅት ከጌዴዎ እና ከጉደር፤ ከጀልዱ አካባቢ ሪፈር የሚባሉት ወደ አምቦ ሪፈራል ሆስፒታል እንጂ እንደድሮው ወደ አምቦ አጠቃላይ ሆስፒታል ባለመሆኑ መጨናነቁን ቀንሶታል፡፡ ነገር ግን አሁን ትንሽ ይሻላል ቢባልም ያው ችግሩ እንዳለ ነው፡፡ በአምቦ አጠቃላይ ሆስፒታል በአሀኑ ወቅት በወር የሚወልዱት እናቶች ወደ 178/አንድ መቶ ሰባ ስምንት የሚደርስ ሲሆን የአለው የአልጋ ቁጥር ግን 4/አራት እንዲሁም ኮች 4/አራት ብቻ ነው፡፡ በሆስፒታሉ ላይ ጫና የሚፈጥሩት በግላቸው ፈልገው የሚመጡት ታካሚዎች ናቸው፡፡ እነዚህ ወላዶች በአብዛኛው ምንም የጤና ችግር የሌለባቸው እና በአቅራቢያቸው ባሉ የጤና ጣቢያዎች ሊወልዱ የሚችሉ ሆነው ሳለ ወደአምቦ አጠቃላይ ሆስፒታል በመምጣት የአልጋም ሆነ የባለሙያውን ኃይል እንዲጣበብ ያደርጉታል። ሆስፒታሉ ይበልጥ ከወሊድ ጋር በተያያዘ በሚፈጠሩ የጤና እክሎች በተቸገሩት ላይ ብቻ ቢያተኩርና ቢሰራ ጫናው ይቀንሳል የሚል እምነት አለ፡፡ ስለዚህም ጤነኛዎቹ ወላዶች እናት በምንም ሁኔታ ወደሆስፒታሉ ስትመጣ አንቺ ጤነኛ ወላድ ነሽና ተመለሽ እንደማይባል ስለሚያውቁ ብቻ  በሆስፒታሉ አሰራር ላይ ችግር ከማስከተል ቢቆጠቡ መልካም ነው፡፡
ጥ/    ወደሆስፒታሉ የሚመጡት እናቶች ይበልጡኑ የሚታዩባቸው ሕመሞች ምንድናቸው?
መ/    በሪፈርም ይሁን በግላቸው ወደሆስፒታሉ ለእርዳታ የሚመጡት እናቶች በአብዛኛው የሚታይባቸው ችግር በጤና ጣቢያም ይሁን በቤታቸው በረጅም ጊዜ ምጥ የተነሳ የማህጸን መፈንዳት እንዲሁም ከደም ግፊት ጋር በተያያዘ ኢክላምፕሲያ የመሳሰሉት በተጨማሪም ከወሊድ በሁዋላ የደም መፍሰስ ችግሮች ይገጥሙዋቸዋል፡፡ የማህጸን መፈንዳት ደርሶባቸው የሚመጡት በጽንሱ ላይ ጉዳት ደርሶ እናትየውንም ከሚያሰጋበት ደረጃ ላይ ሆነው ከሆስፒታል ሲደርሱ በከፍተኛ ርብርብ እናትየውን ለማዳን ሙከራ ይደረጋል፡፡
በመቀጠል ሀሳብዋን ያብራራችልን ነርስ ሲስተር ስንታየሁ አሰፋ ትባላለች፡፡ ሲስተር ስንታየሁ በእናቶችና በሕጻናት ጤና ላይ የምትሰራ ባለሙያ ነች፡፡
ጥ/  ከኤችአይቪ ጋር በተያያዘ ለእናቶች የሚሰጠው አገልግሎት ምን ይመስላል?
መ/    እናቶች በእርግዝናቸው ወቅት ለክትትል ሲመጡ አስቀድሞ የምክር አገልግሎት በመስጠት ምርመራ እንዲያደርጉ ደረጋል፡፡ ከአሁን ቀደም በሌላ ሆስፒታልም ይሁን በአምቦ አጠቃላይ ሆስፒታል ተመርምረው እራሳቸውን የሚያውቁ ቢሆንም እንኩዋን ከእርግዝናው ጋር በተያያዘ ምን ማድረግ እንዳለባቸው ምክር እና አገልግሎቱን እንዲያገኙ የተቻለው ሁሉ ይደረጋል፡፡ ስለዚህም ቫይረሱ በደምዋ ውስጥ ያለባት አዲስ ተመርማሪ ስትገኝ ወዲያውኑ መድሀኒት እንድትጀምር ትደረጋለች፡፡ ቫይረሱ በደማቸው ውስጥ ያለባቸው እናቶች በሚወል ዱበት ጊዜ ወዲያውኑ Nevirapine የተሰኘውን መድሀኒት እንዲጀምሩ ይደረጋል፡፡  ከዚያም ሕጻናቱ በምንም መንገድ ቫይረሱ ከእና ታቸው እንዳይተላለፍባቸው ለማድረግ በሳይንሱ ረገድ የተቀመጠውን መስፈርት በሙሉ ለማሟላት ጥረት ይደረጋል፡፡
ጥ/    የትዳር ጉዋደኞች ስለሁኔታው ያላቸው ምላሽ ምንይመስላል?
መ/    ቀደም ሲል ቫይረሱ በደማቸው መኖሩን ያወቁ እናቶች ባሎቻቸውም ሁኔታውን የተረዱ በመሆኑ ምንም ችግር አይገጥምም፡፡ነገር ግን አዲስ ተመርማሪ ከሆነችና ቫይረሱ በደምዋ ውስጥ መኖሩን ገና ያወቀች ሴት ከሆነች ባለቤትዋን እንድትጠራ ወረቀት ይሰጣታል፡፡ ብዙዎቹ ባሎች ግን ወደሆስፒታል ለመቅረብ ፈቃደኛ አይሆኑም። አን ዳንዶቹም ቢመጡ እንኩዋን ተጣ ልተው አንዳንድ ጊዜ በሚስቶቻቸው ላይ ዱላ የሚ ሰነዝሩም አይጠፉ። ቢመጡም በትክክል ምር መራውን ለማድረግ ፈቃደኛ የማይ ሆኑበት አጋጣሚ ብዙ ነው፡፡ ውጤቱም አንዳንዴ ቫይረሱ በደማ ቸው የሚገኝ ሲሆን አንዳንዴ ደግሞ ወንዶቹ ቫይረሱ በደማቸው አይገኝም፡፡ በሆስፒታሉ በኩል ግን ሁለቱም ማለትም ባልና ሚስቱ ያሉበትን የጤና ሁኔታ አውቀው በወደፊት ሕይወታ ቸው ማድረግ ያለባቸውን ነገር ይመከራሉ፡፡  
አዋላጅ ነርስ በሱፈቃድ እንደሚገልጹት ወላድ እናቶችን በሚመለከት ያሉት መዘግየቶች አሁንም እንደሚንጸባረቁ ነው፡፡ አንዳንዶች ከመንገድ እርቀው ስለሚኖሩ ብዙ ጊዜ ምጥ ሲይዛቸው በፍጥነት ወደ ጤና ተቋም ለመሄድ ይቸገራሉ። ስለዚህም ከቤታቸው ወልደው ችግር ገጥሞአቸው ለሕክምናው ይመጣሉ፡፡ ከዚህም በተጨማሪ የአምቡላንስ አጠ ቃቀሙ ላይ ምናልባት ዘግይተው አምቡላንስ እንዲመጣ መጠየቅ ወይንም አምቡላንሶ ተጠርቶ በተለያዩ ምክንያቶች በፍጥነት አለመድረስ የመሳሰሉት ችግሮች እናቶቹን ወደሆስ ፒታል ከመምጣት ሊያዘገዩአቸው ይችላሉ፡፡ አንዳንድ ጊዜ በደረሱበት ጤና ጣቢያም አገልግሎት አሰጣጡ ላይ አንዳንድ ችግሮች …ለምሳሌም እንግዴ ልጁን ማዋለድ አለመቻል የመሳሰሉት ችግሮች ገጥሞአቸው እናቶች ሪፈር ሊባሉ ይችላሉ፡፡ ስለዚህም ከእናቶች ጋር በተያያዘ አንድም ቸል ሊባል የሚገባው ነገር የለም፡፡ ለእናቶች የሚሰጠውን አገልግሎት በሚ መለከት ሁሉም ነገር ትኩረትን ይሻል፡፡


    የሰሜን ጎንደር ዞን ዋና ከተማ በሆነችው ደባርቅ ከተማ የኪነ ጥበብ፣ የቱሪዝምና የኢንቨስትመንት ፎረም እንደሚካሄድ ተገለፀ፡፡ ከፎረሙ ጎን ለጎን ዘንድሮ ተማሪዎችን ተቀብሎ ማስተማር የጀመረው ደባርቅ ዩኒቨርሲቲም እንደሚመረቅ የዝግጅቱ አስተባባሪ ሀገሬ ሚዲያና ኮሚዩኒኬሽን ለአዲስ አድማስ አስታውቋል፡፡
በቅርቡ በተደረገው ድልድል የሰሜን ጎንደር ዞን ዋና ከተማ ደባርቅ፤ የአገራችን አስደናቂ ተራሮች ስነ ምህዳር መገኛ፣ የጥንታዊና ታሪካዊ መስህቦች ምድር ስትሆን፣ በዩኔስኮ የተመዘገበው ብቸኛው ፓርካችንን ጨምሮ በርካታ ተፈጥሯዊ፣ መንፈሳዊና ታሪካዊ መስህቦች ይገኙባታል። ፎረሙም ይህን ተፈጥሮ ይበልጥ ለማስተዋወቅና ምቹ የኢንቨስትመንት ሁኔታዎችን ለመፍጠር መዘጋጀቱም ተገልጿል፡፡
ከሚያዚያ 13-15 ቀን 2010 ዓ.ም በሶስቱ ቀናት ትልቅ የኪነ ጥበብ ትርኢት፣ በአስቸጋሪው የሊማሊሞ መንገድ ላይ ሩጫ እንዲሁም በዞኑ የተፈጥሮ ሀብቶች ዙሪያ ጥናታዊ ፅሁፎችና ውይይቶች የሚካሄዱ ሲሆን ታዋቂ የሙዚቃና የቴአትር አርቲስቶች የአካባቢው ተወላጅ ኢንቨስተሮች፣ ከፍተኛ የፌደራልና የክልል የመንግስት ባለሥልጣናት፣ ከአገር ውስጥና ከውጭ ጥሪ የተደረገላቸው እንግዶች በፎረሙ ላይ ይታደማሉ ተብሎ ይጠበቃል፡፡ ሰሜን ጎንደርን ለማልማት በጋራ እንሩጥ” በሚል መርህ በሚዘጋጀው በዚህ ፎረም የሰሜን ጎንደር ዞን የአስተዳደር ህንፃ ግንባታ የመሰረት ድንጋይ ይቀመጣል ተብሎ ይጠበቃል፡፡

Saturday, 14 April 2018 14:47

ጲላጦስ

  (የፍርደ ገምድሎች እንጦሮጦስ!)
        ይህን ሰው ስለ ምን ትከሱታላችሁ? አላቸው። (ዮሐ. 18፡29)
        በዚህ ሰው አንድ በደል ስንኳ አላገኘሁበትም አለ። (ሉቃስ 23፡4)

    (ካለፈው የቀጠለ)
3 - ዥዋዥዌ
በእርግጥም ጲላጦስ አለቅጥ እንዲንገጫገጭ ሆኖ ነበር...
  . . . አስቀድሞ ፤ (ዮሐ. 18፡31-32) . . . እናንተ ወስዳችሁ እንደ ሕጋችሁ ፍረዱበት አላቸው። አይሁድም ለእኛስ ማንንም ልንገድል አልተፈቀደልንም አሉት፤ ኢየሱስ በምን ዓይነት ሞት ሊሞት እንዳለው ሲያመለክት የተናገረው ቃል ይፈጸም ዘንድ ነው። (ወንጀለኞችን በስቅላት ቅጣት መግደል ሮማዊያኑ ወደ ቅድስቲቱ ምድር ያመጡት አዲስ ባህል በመሆኑ፤ የኢትዮጵያ መጽሐፍ ቅዱስ ማኅበር - የመጽሐፍ ቅዱስ መዝገበ ቃላት ገጽ 82 - ስቅለት - ነገር ግን እስራኤላውያን ሰውን በስቅላት አይገድሉም ነበር፤ ዘዳ 21፡21-23/ኢያሱ 10፡26)
በኋላም፤ ጲላጦስ ‹‹የአይሁድን ንጉሥ ልፈታላችሁ ትወዳላችሁን?›› ብሎ አማራጭ ሲያቀርብም፤ እግረ መንገድ አሁንም ከኢየሱስ ያጣውን ምላሽ ለማሟላትና ያንኑ ሮማዊያኑን የሚያባትታቸውን የንጉሥነቱን ጉዳይ ከሕዝቡም እያውጣጣ (investigate እያደረገ) ነበር፡፡ በተለይም በዮሐንስ ወንጌል እንደምናነበው፤ ጲላጦስ የኢየሱስን ፖለቲካዊ ‹አዝማሚያ› ለማወቅ አስልቶ ነበር ይላሉ፤ የታሪክ ተመራማሪያኑ፡፡ Pilate carefully questioned the prisoner about His political roll.
እውነትም ከዚያ ሁሉ ጥያቄና መልስ በኋላ አሁንም ለኢየሱስ ያንኑ ጥያቄ ደግሞ ያቀርብለታል . . .
ጲላጦስም፡- እንግዲያ ንጉሥ ነህን? አለው። ኢየሱስም መልሶ፦ እኔ ንጉሥ እንደ ሆንሁ አንተ ትላለህ። እኔ  ስለ እውነት ልመሰክር ስለዚህ ተወልጃለሁ ስለዚህም ወደ ዓለም መጥቻለሁ፤ ከእውነት የሆነ ሁሉ ድምፄን ይሰማል አለው። ጲላጦስ፡- እውነት ምንድር ነው? አለው። (ምናልባት የጲላጦስ እውነት ንጉሡን ከማገልገል ያለፈ ስላልነበረ ይሆንን?) ይህንም ብሎ ዳግመኛ ወደ አይሁድ ወጥቶ እኔስ አንዲት በደል ስንኳ አላገኘሁበትም። ነገር ግን በፋሲካ አንድ ልፈታላችሁ ልማድ አላችሁ፤ እንግዲህ የአይሁድን ንጉሥ ልፈታላችሁ ትወዳላችሁን? አላቸው። ሁሉም ደግመው በርባንን እንጂ ይህን አይደለም እያሉ ጮኹ። በርባን ግን ወንበዴ ነበረ። (ዮሐ. 18፡37-40) እርሱም በፍርድ ወንበር ተቀምጦ ሳለ፣ ሚስቱ ስለ እርሱ ዛሬ በሕልም እጅግ መከራ ተቀብያለሁና በዚያ ጻድቅ ሰው ምንም አታድርግ ብላ ላከችበት። (ማቴ.27፡13-19) (ጲላጦስ ግን የሚስቱን ምክር አልሰማም፡፡ ሆኖም ግን አሁንም በኢየሱስ ላይ ለመፍረድ ዝግጁ አይደለምና ደግሞ ይጠይቃል) በርባንን ወይስ ክርስቶስ የተባለውን ኢየሱስን ማንኛውን ልፈታላችሁ ትወዳላችሁ? አላቸው፤ በቅንዓት አሳልፈው እንደ ሰጡት ያውቅ ነበርና። (ግን ይህን ራሱ የሚያውቀውንም ውስጡን አልሰማም)... በዚህ ሰው አንድ በደል ስንኳ አላገኘሁበትም አለ። (ሉቃስ 23፡4) ገዢውም፤ ምን ነው? ያደረገው ክፋት ምንድር ነው? አለ (ማቴ. 27፡23)
(እስከ መጨረሻው ቅጽበት ኢየሱስን ሊፈታው መፈለጉን እናስተውላለን፤ግና እርሱ ራሱ የወደደውንም አላደረገም፡፡ ወደ መጨረሻም ከከሳሾቹ ድምጽ ውስጥ ያስተጋባው አንዳች አስገምጋሚ ምላሽ ሳያናውጠው አልቀረም፡፡)
...ራሱን የእግዚአብሔር ልጅ አድርጎአልና አሉት። ስለዚህ ጲላጦስ ይህን ነገር በሰማ ጊዜ እጅግ ፈራ፤ ተመልሶም ወደ ገዢው ግቢ ገባና ኢየሱስን አንተ ከወዴት ነህ? አለው። ኢየሱስ ግን አንድ እንኳ አልመለሰለትም። ስለዚህ ጲላጦስ አትነግረኝምን? ልሰቅልህ ሥልጣን እንዳለኝ ወይም ልፈታህ ሥልጣን እንዳለኝ አታውቅምን ? አለው። ኢየሱስም መልሶ፦ ከላይ ካልተሰጠህ በቀር በእኔ ላይ ምንም ሥልጣን ባልነበረህም፤ ስለዚህ ለአንተ አሳልፎ የሰጠኝ ኃጢአቱ የባሰ ነው አለው። ከዚህ በኋላ ጲላጦስ ሊፈታው ፈለገ፤ ነገር ግን  . . . (ዮሐ. 19፡7-12)
(ፍፁም ባልጠበቀው መንገድ በስጋት የሚንጥና የሞት ፍርድ ውሳኔውን ከማሳለፍ ወዴትም ውልፍት ማለት የማያስችለው ወጥመድ ፊቱ ተደቀነበት! . . .)
...ይህንስ ብትፈታው የቄሣር ወዳጅ አይደለህም፤ ራሱን ንጉሥ የሚያደርግ ሁሉ የቄሣር ተቃዋሚ ነው እያሉ ጮኹ።
በርግጥም ያኔ፤ ጲላጦስ ክፉኛ ክው ያለ እናም በቃ በእጅጉ የተንገጫገጨ አሳዛኝ ሰው የሆነ ይመስላል፡፡ በደካማ ጎኑ ነበር የመጡበት፡፡ አዎን! ማንም ቢሆን በዚህ መሰል ሁኔታ ውስጥ ራሱን ቢያገኘው፤በዚያች ወሳኝ ፍትሀዊ የፍርድ ውሳኔ የማሳለፊያ ቁርጥ ጊዜ ላይ በፍርድ ወንበሩ ቢቀመጥ ላፍታም ቢሆን  ይዋልላል፡፡ ግን ደግሞ ሁለት አማራጭ ይኖረዋል፤ ወይ ከአለት የጸና የልዕለ ሰብዕና ካባ የሚያጎናጽፈውን እውነት ጠብቆ ለእውነቱና ለራሱ ህሊና ታማኝ መሆን ይችላል ወይም ደግሞ ህሊናውን እየቧጠጠ ለሚያደማ ሀሰት ተገዝቶ፣ የአዕምሮ እረፍቱን አሟጥጦ ደፍቶ፣ ሰላምና ክብሩን አጥቶ፣ እስከ ዘላለሙ ንፁህ ሰብእናውን አጉድፎ ከራሱ ከማንነቱና ከመላው ሕዋ ጋርም ተቆራርጦ ያርፈዋል። ውሳኔው ቀላል አይደለም፡፡ እናስ እሺ ጲላጦስ ምን ሊል ይችላል... ‹‹አሁን ባይኔ መጣሽ!››  እንዴ! ለምን ምንም ነገር ጥንቅር ብሎ አይቀርም፤የንጉሡን ወዳጅነት አጥቶ ከመኖር፡፡ ህእ!›› (‹‹የምኖረው ለማን ሆነና!›› አይነት፡፡)
...በዚህ አተያይ/ መላምት ዙሪያ ያጠነጠኑት የታሪክ ተመራማሪዎቹም ይህን አሻሚ የኢየሱስ ከሳሾች አቀራረብ፤ የጲላጦስን የዳኝነት አቋም እሁለት ቦታ የከፈለ (explicit threat against Pilate) ፈተና ነበር ይሉታል ፡፡
ጲላጦስ፤ በኢየሱስ ላይ ባሳለፈው ፍርዱም ለንጉሡ ስሞታ ቀርቦበት እንደለመደው ከምርመራ ጥያቄ ቢያመልጥም፤ በኋለኞቹ ተደጋጋሚ ስህተቶቹ ምክንያት ግን ወደ ሮማ መጠራቱ አልቀረለትም፡፡
4 - የፍርድ ጥፍር
‹‹ህማማት ነውና የይሁዳን ታሪክ ልንገርህ...›› ይለናል፤ የኔታ ስብሀት ለአብ ገብረ እግዚአብሔር በ567 ድርሰቱ ውስጥ አምስት ልጆቹንና ስድስተኛ ሚስቱን በረሀብ ሞት ተነጥቆ፣ 7ኛ አንድ እሱ ብቻውን ቀርቶ እብደት ባናወዘውና ታማኙን የእርሻ በሬውን አርዶ በመብላቱ ራሱን በአስቆሮቱ ይሁዳ በመሰለው ገጸ ባሕርይው አንደበት፡፡... ‹‹ ይሁዳ ከዳተኛ ነው ይላሉ፣ የኔን ታሪክ ያልሰሙ፡፡ ይሁዳ እንኳ ተጸጸተ፤ ተሰቀለ፤ ራሱን ገደለ፤ እኔ ግን! እኔ ግን! ወይኔ! ወይኔ! ወይኔ!
ይህ ድምጽ በሀገረ ገዢው፣ በተንገጫገጨው ዳኛ ልቦናም ውስጥ ያለማቋረጥ መጎሰሙ አይጠረጠርም፡፡
ጲላጦስ፤ ከቄሣሩ ጋር ሲገናኝ የቀረቡበትን ስሞታዎች ሁሉ በወዳጅነት መንፈስ ሊያስተባብል ይቻለዋልና እምብዛም አያሳስበውም፤ ምናልባትም በታማኝነትና ፍጹም ታዛዥነት ለአስር ዓመታት በጽናት ላበረከተው አገልግሎቱ ከንጉሡ ዘንድ ውዳሴና ሹመትም ሳይጠብቅ አይቀርም፡፡ አሳዛኙ ነገር ግን ጲላጦስ ሀገሩ ሲደርስ፤ እንዲያ አቅሉን እስኪስት ጠብ እርግፍ ያለለት ጌታው ጢባርዮስ ቄሣር ሞቶ ነበር። ይህም ብቻ አይደል፤ ጲላጦስ ገፍቶት/ ሰቅሎት የመጣው ክርስትናም ትንሣኤ አድርጎ በራሱም ምድር ዙሪያ ቀድሞት መድረሱንና ዘሩ ማጎንቆል መጀመሩን በገነገነ ጊዜ፤ (በጲላጦስ ፊት የካዳችሁትን ብላቴናውን ኢየሱስን አከበረው። ሐዋ.3፡13) በምርመራው ፍጻሜ በVienna-on-Rhone  በግዞት ሳለ ፤ ሁለመናውን እንደ ረመጥ እየፈጀ እሚያብከነክነው በኢየሱስ ላይ ያሳለፈው ፍርድ ሌት ተቀን እረፍት ስለነሳው፤  ጲላጦስም የከሀዲውን የይሁዳን ጽዋ ጨለጣት፡፡ ... ኢየሱስን አሳልፎ የሰጠው ይሁዳ እንደ ተፈረደበት አይቶ ተጸጸተ፥...ብሩንም በቤተ መቅደስ ጥሎ ሄደና ታንቆ ሞተ። (ማቴ. 27:3/5) ጲላጦስም እንዲሁ ‹‹የቤተ መንግሥት ክብሩን ጥሎ›› ራሱን ገደለ፡፡
ከቶ አይቀርም ሞቱ
ምንም ቢታክቱ
ምን ቢሰነብቱ፡፡
 (የሕዝብ ግጥም - በገና፡፡)
5 - ባርነት ወ ነጻነት
‹‹ሰማይና ምድር ያልፋሉ ቃሌ ግን አያልፍም።›› እንዲል መጽሐፍ፤ አልፋና ኦሜጋ ኗሪው ህያው ቃል፣ ስለ ፍጥረት ባርነት እና ስለ እግዚአብሔር ነጻነት፣ ክብር፣ተስፋ፣ ምህረት፣ ሕግ እና ፍርድ ...ያበረከተልንን የሕይወት ስንቅ አስታውሰን እናሳርግ ...ሰዎች ነንና ከኃጢዐት ፈተና ባናመልጥም፣ እንደ ስራችን ሳይሆን እንደ ፀጋና ቸርነቱ ማስተዋሉን ቢያድለን እንማርበት ዘንድ፤ ከልብ እውነቱ የተፋታ፣ ለሌሎች በባርነት ተኮድኩዶ፣ ላላመነበት እውነት አጎብድዶ ራሱን የካደ ሰው ያመሻሽ እድሜ ዘመን እርቃኑን ሲቀር ምን እንደሚመስል የምስኪኑ ፈራጅ አሳዛኝ ገድል ጥሩ ማሳያ ነውና ከጲላጦስ ከንቱ ፀፀት ያትርፈን፡፡ ሁሉ ከንቱ ከንቱ፡፡ እነሆ . . . (ሮሜ  8:20-21) ፍጥረት ለከንቱነት ተገዝቶአልና፥ በተስፋ ስላስገዛው ነው እንጂ በፈቃዱ አይደለም፤ ተስፋውም ፍጥረት ራሱ ደግሞ ከጥፋት ባርነት ነጻነት ወጥቶ ለእግዚአብሔር ልጆች ወደሚሆን ክብር ነጻነት እንዲደርስ ነው። (ገላትያ 5፡1) በነጻነት ልንኖር ክርስቶስ ነጻነት አወጣን፤ እንግዲህ ጸንታችሁ ቁሙ እንደ ገናም በባርነት ቀንበር አትያዙ። (የያዕቆብ መልእክት 2፡12-13) በነጻነት ሕግ ፍርድን ይቀበሉ ዘንድ እንዳላቸው ሰዎች እንዲህ ተናገሩ፥ እንዲህም አድርጉ። ምሕረትን ለማያደርግ ምሕረት የሌለበት ፍርድ ይሆናልና፤ ምሕረትም በፍርድ ላይ ይመካል።
አሜን ፡፡
መልካም ዳግማይ ትንሣኤ!!