Administrator

Administrator

 ሰሜን ኮርያ ባለፈው ሳምንት ብቻ ከ400 በላይ ዜጎቿ በክሎሪን ጋዝ ጥቃት ለሞት ለተዳረጉባትና በእርስበርስ ጦርነት አሰቃቂ ውድመት እያስተናገደች ለምትገኘው ሶርያ፤ ባለፉት አምስት ዓመታት 40 ጊዜያት ያህል፣ ለኬሚካል ጦር መሳሪያዎች ምርት በጥሬ እቃነት የሚውሉ ቁሳቁሶችን መሸጧን ተመድ አስታውቋል፡፡
ሰሜን ኮርያ እ.ኤ.አ ከ2012 እስከ 2017 በነበሩት ዓመታት፣ አለማቀፍ ማዕቀቦችን በመጣስ፣ ለኬሚካል ጦር መሳሪያዎች ምርት የሚውሉ ጥሬ ዕቃዎችን ወደ ሶርያ መላኳንና የአገሪቱ የሚሳኤል ባለሙያዎችም፣ በሶርያ የጦር መሳሪያ ማምረቻ ማዕከላት ውስጥ ሲንቀሳቀሱ እንደነበር የሚያረጋግጥ መረጃ ማግኘቱን፣ተመድ ባወጣው መረጃ ማስታወቁን ቢቢሲ ዘግቧል፡፡
ሶርያ ከሰሜን ኮርያ ለገዛቻቸው ለእነዚህ ጥሬ ዕቃዎች፣ “ሳይንቲፊክ ስተዲስ ኤንድ ሪሰርች ሴንተር” የተባለው የሶርያ መንግስት ተቋም፣ በሌሎች ኩባንያዎች ስም ክፍያ መፈጸሙን አረጋግጫለሁ ያለው ተመድ፤ተቋሙ የተመሰረተው ለምርምር ቢሆንም በሶስት ማዕከላት ውስጥ የኬሚካል ጦር መሳሪያዎችን ሲያመርት እንደነበር መረጋገጡንም ዘገባው አመልክቷል፡፡

ኢንፌክሽን፣ የወሊድ ችግሮችና ካለወቅቱ መወለድን ጨምሮ በተለያዩ ምክንያቶች በአለማችን በየአመቱ 2.6 ሚሊዮን ያህል ህጻናት በተወለዱ በአንድ ወር ጊዜ ውስጥ እንደሚሞቱ የተባበሩት መንግስታት የህጻናት መርጃ ድርጅት ዩኒሴፍ አስታውቋል፡፡
በፈረንጆች 2016 በአለማችን አገራት የተከሰቱ መሰል የህጻናት ሞት ክስተቶችን በማጥናት የአገራቱን የችግሩ ተጠቂነት ደረጃ ባለፈው ማክሰኞ ይፋ ባደረገው ሪፖርት ያወጣው ድርጅቱ፤ በከፋ ደረጃ ላይ በመገኘት ቀዳሚ በሆነቺው ፓኪስታን በአመቱ ከተወለዱ ህጻናት በአማካይ ከ22ቱ አንዱ ዕድሜው አንድ ወር ሳይሞላው መሞቱን አመልክቷል፡፡
ከጃፓን በመቀጠል በርካታ ህጻናት በተወለዱ በአንድ ወር ጊዜ ውስጥ የሚሞቱባቸው የአለማችን አገራት ተብለው በሪፖርቱ የተጠቀሱት ማዕከላዊ አፍሪካ ሪፐብሊክና አፍጋኒስታን ሲሆኑ ሶማሊያ፣ ሌሴቶ፣ ጊኒቢሳኦ፣ ደቡብ ሱዳን፣ ኮትዲቯር፣ ማሊና ቻድ በቅደም ተከተላቸው እስከ አስረኛ ያለውን ደረጃ ይዘዋል፡፡
ከአለማችን አገራት ለመሰል ችግር በመጋለጥ የመጨረሻውን ደረጃ በያዘቺው ጃፓን፣ በአመቱ ከተወለዱ እያንዳንዳቸው 1ሺህ 111 ጨቅላዎች በአማካይ አንዱ ብቻ ለህልፈተ ህይወት መዳረጉን ያስታወሰው ሪፖርቱ፤ ከጃፓን በመቀጠል አይስላንድና ሲንጋፖር ዝቅተኛ የህጻናት ሞት ያለባቸው የአለማችን አገራት እንደሆኑ ጠቁሟል፡፡
በቀዳሚዋ ፓኪስታንና በመጨረሻዋ ጃፓን መካከል ያለውን የችግሩ ተጠቂነት ደረጃ ያነጻጸረው ሪፖርቱ፤ በፓኪስታን የሚወለድ አንድ ህጻን በጃፓን ከሚወለድ ሌላ ህጻናት ጋር ሲነጻጸር የአንድ ወር እድሜውን ሳይሞላ ለህልፈተ ህይወት የመዳረግ እድሉ በ50 እጥፍ ያህል የጨመረ እንደሆነ አብራርቷል፡፡

 የአፍሪካ አገራት ህገወጥ የሰዎች ዝውውር፣ የነዳጅ ዝርፊያ፣ የአደንዛዥ እጽ ንግድና ኮንትሮባንድን በመሳሰሉ ተግባራት በሚፈጸሙ ህገወጥ የገንዘብ ዝውውሮች በየዓመቱ በድምሩ 50 ቢሊዮን ዶላር ያህል እንደሚያጡ ተዘገበ፡፡
ተቀማጭነቱ በፓሪስ የሆነው አለማቀፉ የኢኮኖሚና የልማት ትብብር ተቋም ከሰሞኑ ያወጣውን ሪፖርት ጠቅሶ ሲኤንኤን እንደዘገበው፣ በምዕራብ አፍሪካ አገራት ከሚከናወነው ህገወጥ የገንዘብ ዝውውር 80 በመቶውን የሚይዘው ከተፈጥሮ ሃብት በተለይ ደግሞ ከነዳጅ ዝርፊያ ጋር የሚያያዝ ነው፡፡
በአፍሪካ አገራት በህገ ወጥ መንገድ የሚዘዋወረው የገንዘብ መጠን ከፍተኛ መሆኑ የአገራቱን ልማት እንዳይፋጠን ከፍተኛ እንቅፋት መፍጠሩን የጠቆመው ዘገባው፤በአውሮፓ አገራትም በህገወጥ የሰዎች ዝውውር እጅግ ከፍተኛ ገንዘብ እንደሚንቀሳቀስ አመልክቷል፡፡

ባሳለፍነው ሳምንት በይፋ ተመርቆ የወጣውና አፍሪካዊ ፊልም ባህር የመሻገር ብቃት የለውም የሚለውን አመለካከት እንዳከሸፈ የተነገረለት “ብላክ ፓንተር” ፊልም፣ ገና ለእይታ በበቃ በአራት ቀናት ውስጥ ብቻ 241.9 ሚሊዮን ዶላር ገቢ ያገኘ ሲሆን፣ በዚህ ገቢውም ከ”ስታር ዎርስ” ቀጥሎ በመቀመጥ ታሪክ ሰርቷል፡፡
ወንጀልን ለመታገል ቆርጦ በተነሳ የአንዲት ምናባዊ የመካከለኛው አፍሪካ አገር መሪ የስኬት ጉዞ ላይ የሚያጠነጥነውና በጥቁሩ ዳይሬክተር ሪያን ኮግለር የተሰራው “ብላክ ፓንተር”፤ ለእይታ በበቃ በቀናት እድሜ ውስጥ በርካታ የቦክስ ኦፊስ ክብረ-ወሰኖችን መሰባበሩን ተያይዞታል፡፡ ባለፈው ሳምንት ብቻ በትዊተር ማህበራዊ ድረገጽ ከ5 ሚሊዮን በላይ ፊልሙን የተመለከቱ ጽሁፎችና መልዕክቶች የተሰራጩለት ፊልሙ፤ በአለማችን ታሪክ በትዊተር እጅግ በርካታ ቁጥር ያላቸው ተጠቃሚዎችን  ያነጋገረ ቀዳሚው ፊልም ሆኗል፡፡
ፊልሙ ከአሜሪካ የቦክስ ኦፊስ የደረጃ ሰንጠረዥ በተጨማሪ በእንግሊዝ፣ አየርላንድ፣ ቻይና፣ ሩስያ፣ ጃፓንና ሌሎች በርካታ የአለማችን አገራት የፊልሞች ገበያና የገቢ የደረጃ ሰንጠረዦች የሚደንቅ ክብረ ወሰን እየጨበጠ እንደሚገኝ አሶሼትድ ፕሬስ ዘግቧል፡፡ በሆሊውድ መንደር ባልተለመደ ሁኔታ አፍሪካውያንን ባለስኬት ጀግኖች አድርጎ የሚያሳየው ይህ ፊልም፣ የቀድሞዋ የአሜሪካ ቀዳማዊት አመቤት ሚሼል ኦባማን ጨምሮ አለማቀፍ ዝነኞች በአደባባይ አድናቆታቸውን እየቸሩት ነው ሲል ቢቢሲ ዘግቧል፡፡
“ብላክ ፓንተር” 200 ሚሊዮን ዶላር ያህል ወጪ እንደተደረገበት የዘገበው አሶሼትድ ፕሬስ፤ በታሪክ ከፍተኛው በጀት የተመደበለት በጥቁር ጀግኖች ዙሪያ የሚያጠነጥንና በአብዛኛው ጥቁር የፊልም ባለሙያዎችን ያሳተፈ ቀዳሚው ፊልም እንደሆነ አመልክቷል፡፡

 ለረጅም ዓመታት ልደታቸውን በብሄራዊ በዓልነት እጅግ በደመቀ ሁኔታ ከህዝባቸው ጋር በአደባባይ ሲያከብሩ የኖሩት የቀድሞው የዚምባቡዌ ፕሬዚዳንት ሮበርት ሙጋቤ፤ ባለፈው ረቡዕም የ94ኛ አመት ልደታቸውን ከወትሮው በፈዘዘ መልኩ እንደነገሩ አክብረዋል፡፡
ሙጋቤ ምንም አንኳን ስልጣን ከለቀቁ ወራትን ቢያስቆጥሩም፣ የልደት በዓላቸው ግን የዚምባቡዌ ወጣቶች ቀን በሚል ስያሜ በብሄራዊ ደረጃ ወጣቶችን ለበጎ ስራ በማሰማራት መከበሩን የዘገበው ኒውስ 24፤ እንደ ወትሮው በኬክና በሻምፓኝ፣ በክምር ስጦታና በደማቅ ሙዚቃ፣ በይፋ በአደባባይ  አለመከበሩን አመልክቷል፡፡
የሙጋቤ ልደት በየአመቱ በመቶ ሺህዎች የሚቆጠር በጀት ተመድቦለት በሚገርም ፈንጠዝያና በግዙፍ ኬክ ይከበር እንደነበር ያስታወሰው ዘገባው፤ፓርቲያቸው ዛኑ ፒኤፍ ግን ከቀናት በፊት ባወጣው መግለጫ የሙጋቤ ልደት ያለ ብዙ ወጪ ቀለል ብሎ እንደሚከበር ማስታወቁን ገልጧል፡፡

 አሜሪካዊቷ የፖፕ ሙዚቃ አቀንቃኝ ማዶና፣ ከማላዊ በማደጎ ወስዳ እያሳደገቺው የሚገኘው የ12 አመቱ ታዳጊ ዴቬድ ባንዳ፤ ወደፊት የአገሪቱ ፕሬዚዳንት እንደሚሆን ያላትን ጽኑ እምነት መግለጧ ተዘግቧል፡፡
ከምታሳድጋቸው ስድስት የማደጎ ህጻናት መካከል አንዱ የሆነው ማላዊው ዴቪድ ባንዳ፣ እጅግ የሰላ አስተሳሰብና የአእምሮ ብቃት የተላበሰ ታዳጊ እንደሆነ ከሰሞኑ በትዊተር ድረገጽዋ ላይ በጻፈቺው ጽሁፍ የጠቆመቺው ማዶና፤ ለወደፊት እድሜው ሲገፋ አገሪቱን በብቃት የሚመራ ታላቅ ሰው እንደሚሆን በጽኑ አምናለሁ ማለቷን ቢቢሲ ዘግቧል፡፡
ዴቪድ ባንዳን ጨምሮ ከማላዊ አራት ህጻናትን በማደጎ ወስዳ እያሳደገች እንደምትገኝ የጠቆመው የቢቢሲ ዘገባ፤ ከ12 አመታት በፊት ባቋቋመቺው ሬዚንግ ማላዊ የተሰኘ ግብረ ሰናይ ድርጅት አማካይነት የተለያዩ ድጋፎችን እያደረገች እንደምትገኝም አውስቷል፡፡
የአገሪቱ መንግስት ከ5 አመታት በፊት ማዶና በአለም አደባባይ ለአገራችን የምታበረክተውን አስተዋጽኦ ከሚገባው በላይ አጋንና በመናገር ላይ ናት በሚል ወንጅሏት እንደነበርም ዘገባው አስታውሷል፡፡

 በደራሲ አንድነት ሀይሉ የተዘጋጀው “ቋንቋ እውቀት አይደለም” የተሰኘ መፅሐፍ ሰሞኑን ለንባብ በቃ፡፡ ደራሲው፤ “ሁሉም ሰው ውስጥ ሁሉም ቋንቋ አለህ ቋንቋ አለህ ቋንቋ እውቀት አይደለም፤ እውቀት ግን ቋንቋ ነው፡፡ ቋንቋ ሀገር አይደለም፤ ግን እውቀት ግን ሀገር ነው” ይላል- ደራሲው በመፅሐፉ፡፡
በዚህ መፅሐፍ ውስጥ ከተነሱ አያሌ ርዕሰ ጉዳዮች መካከል”የብሄር ጭቆና ምንድ ነው ብሄርስ ምንድ ነው?”፣ “ቱሪዝምና ቋንቋ”፣ “ትምሀርትና ቋንቋ የሚሉት ይገኙበታል፡፡ በ151 ገፆች የተቀነበበው መፅሐፍ በ50 ብር ለገበያ ቀርቧል፡፡

  የ“ወይዘሪት ምድረ ቀደምት” የቁንጅና ውድድር ይደረጋል

   የኢትዮጵያ ብሔር ብሔረሰቦች እርስ በእርስ ይበልጥ ይተዋወቁበታል የተባለለትና አዲሱ የኢትዮጵያ ቱሪዝም መለያ የሆነውን “ምድረ ቀደምት”ን ለማስተዋወቅ ያለመው “ኢትዮ አፍሪካ ካርኒቫል” በግንቦት ወር የመጀመሪያው ሳምንት ላይ እንደሚካሄድ ተገለፀ፡፡
 የኢትዮጵያ የባህልና ቱሪዝም ሚኒስቴር፣ አዲስ አበባ ባህልና ቱሪዝም ቢሮና የኢትዮጵያ ቱሪዝም ድርጅት፣ ከዘጠኙ ክልሎች እንዲሁም ከአይጂ ኢንተርቴይመንትና ከብርሀን ኤቨንት ኦርጋናይዘር ጋር በጋራ በሚያካሂዱት በዚህ ካርኒቫል የ”ምድረ ቀደምት” ሞዴል ሆና በዓለም ብራንዱን የምታስተዋውቅ አምባሳደር ለመምረጥ “የወይዘሪት ምድረ ቀደምት” የቁንጅና ውድድር እንደሚካሄድ ታውቋል፡፡ ክልሎች ለመጨረሻ ዙር ያለፉ አምስት አምስት አሸናፊዎችን ወደ አዲስ አበባ በመላክ የሚያወዳድሩ ሲሆን አሸናፊዋ “ወ/ሪት ምድረ ቀደምት” ሆና እንደምትሾምና ፖስተሯ ተሰርቶ ለአለም እንደምትተዋወቅ፣አዘጋጆቹ ከትላንት በስቲያ ረፋድ ላይ በባህልና ቱሪዝም ሚኒስቴር በሰጡት ጋዜጣዊ መግለጫ ጠቁመዋል፡፡
በዚህ የካርኒቫል ሳምንት “ምድረ ቀደምት አገር ኢትዮጵያ በመወለዴ እኮራለሁ” በሚል መሪ ቃል፣ምድረ ቀደምት ሎጎ የታተመበት ቲ-ሸርት የለበሱ 10 ሺህ ያህል ሰዎች የእግር ጉዞ እንደሚያደርጉም ተገልጿል፡፡ ለሶስት ቀናት የሚቆይ ባዛርና ኤግዚቢሽንም የካርኒቫሉ አንዱ አካል እንደሚሆን የተነገረ ሲሆን በዚህ ባዛር ላይ ብሔር ብሔረሰቦች ምርታቸውን፣ ባህላዊ ምግባቸውን፣ አልባሳትና የንግድ ሥራቸው ለእይታ የሚያበቁበትና ልምድ የሚለዋወጡበት እንደሚሆንም ታውቋል። የመንገድ ላይ ትርኢትን በሚያካትተው በዚህ ካርቪናል፤የተለያዩ ብሔር ብሔረሰቦች ዳንሶቻቸውንና ባህላዊ ጭፈራዎቻቸውን ለተመልካች ያቀርባሉ ተብሏል፡፡ በዚህ የጎዳና ላይ ትርኢት ሥራቸውን እንዲያቀርቡ ሌሎች የአፍሪካ አገራትም እንደሚጋበዙ የተገለፀ ሲሆን በስፔይን አገር በየዓመቱ የሚካሄደው “ሮቶቶም” የተባለው የሬጌ ፌስቲቫል ወደ ኢትዮጵያ መጥቶ፣በምሽቱ በሚያቀርበው የሬጌ ኮንሰርት  ካርኒቫሉ እንደሚዘጋ ለማወቅ ተችሏል፡፡

   (ከሣህለ ሥላሴ ብርሃነ ማርያም)
          ርዕስ፡- መልህቅ
          ደራሲ፡- ዘነበ ወላ
        የሕትመት ዘመን፡- 2010 ዓ.ም
        የትረካ ሥፍራዎች፡ - ምጽዋ ፥ አስመራ ፥ አሰብ ፥ እና አዲስ አበባ በጨረፍታ
        የገጽ ብዛት፡- 448
        ዋጋ፡- 150 ብር


    ይህ መጽሐፍ ልብ ወለድ ነው እንዳንል ጥናት ላይ እንደተመሰረተ ጽሁፍ ዋቢ መጻህፍት ታክለውበታል፤ ያውም በአማርኛና በእንግሊዝኛ የተጻፉ በርካታ መጻሕፍትና ሌሎችም ምንጮች። በሌላ በኩል እውነተኛ ታሪክ ነው እንዳንል አቀራረቡ የታሪክ ሳይሆን የልብ ወለድ ድርሰት የአጻጻፍ ዘዴን ነው የተከተለው፡፡ ታዲያ የድርሰቱ ዓይነት ምንድነው ብለን እንመድበው? ምናልባት ከደራሲው ዘነበ ወላ ጋር በመስማማት፣ በልብ ወለድ መልክ የቀረበ እውነተኛ ሁነት ነው ብንል አያስኬድም ይሆን?
ከቅርብ ጊዜ ወዲህ ከተለመደው የልብ ወለድ አጻጻፍ ዘዴ ወጣ ያሉ ፥ የቤተ ሙከራ ዓይነት ጽሑፎች ብቅ ብቅ ማለት መጀመራቸውን እንገነዘባለን፡፡ ልብ ወለዶች ናቸው እንዳንል አጽመ ታሪክ የሌላቸው፤ በውቅር (“ፕሎት”) ወይም በምክንያትና ውጤት ላይ ያልተመሰረቱ፤ ላይ በላይ እንደ አሸዋ በተከመሩ ሁነቶች ላይ ብቻ የተገነቡ ጽሑፎች ከአንድም ሁለት በላይ መከሰታቸው ተስተውሏል፡፡ “መልህቅ” ከእነዚህ አፈንጋጭ መሰል ጽሑፎች አንዱ ይሁን ወይም አይሁን በእርግጠኝነት ለመናገር ያዳግታል፡፡
ለማንኛውም ይዘቱ በደርግ ዘመን (ሥርዓቱ ተንኮታኩቶ ከመውደቁ ቀደም ባሉት ሁለት ዓመታት) በአስራ አምስቱ ዓመታት ውስጥ በኢትዮጵያ ባህር ኃይል አካባቢ የነበረውን የሕይወት ሁኔታ አጉልቶ የሚያሳይ መጽሐፍ ነው፡፡ በባህር ኃይሉ የነበሩት የጦር መርከቦች ዓይነት፤ የባህረኞቹ (የአዛዦቹና የታዛዦቹ) የሕይወት ዘይቤ፤ የዕለት ተዕለት የተግባር እንቅስቃሴአቸው፤ የቅኝታቸው ጉዞና መልስ፤ የባህሩ መናወጥና መልሶ መርጋት፤ በተለይ በጉዞ ላይ የሚደርሱ ፈተናዎች፤ የየዕለቱ ምግብና መጠጥ፤ አልፎ አልፎ የሚከናወኑት የመዝናኛ ዝግጅቶች፤ የባህረኞች (በተለይም የወጣቶቹ) የወሲብና የፍቅር ሕይወት፤ የአብዮቱ ዘመን ይፈጥረው የነበረው ፍርሃትና ጭንቀት፤ አንዳንድ ባህረኞች ሥርዓቱን መሸከም አቅቷቸው ወደ ባዕድ አገር ለመሰደድ የሚያደርጉት ሙከራ፤ የተፈጥሮ አስደናቂ ክስተቶች፤ በተለይም የአንዳንድ አሳዎች፥ የየብስ ተንፏቃቂ ነፍሳትና አእዋፍ አስገራሚ የሥጋ ተራክቦና የሚከተለው የሕይወት ሕልፈት፤ የአሳዎች ዝርያዎች ዓይነትና ባህርያቸው፤ በአጠቃላይ በባህርና በየብስ የባህረኞችና የሌሎች ፍጡራን ሕይወት ምን እንደሚመስል ፍንትው አድርጎ የሚያሳይ መጽሐፍ ነው - “መልህቅ”፡፡
ዘነበ ወላ በዚህ መጽሐፉ ከቀድሞዎቹ ሦስት መፅሐፎቹ (ህይወት በባህር ውስጥ ፥ ማስታወሻ ፥ እና ልጅነት) በበለጠ ደረጃ ጥንካሬ ያሳየው በገለጻ ኃይሉ ነው ብንል ሞጋች የሚነሳ አይመስለኝም፡፡ ዋቢ እንዲሆን ቀጥሎ ያለውን እንመልከት፤
“ወደ ራስ ዱሜራ ስንቀዝፍ ቀይ ባህር እንደ ራስ ዳሽን ተራራ ይከመራል፡፡ ጀልባችን ባህሩን በርቅሳው ለማለፍ ትጥራለች፡፡ ባህሩ አፍታም ሳይቆይ እንደሊማሊሞ ገደል ይናድና ቁልቁል ወደ መቀመቅ ጅው እንላለን፡፡ ከላይ ውሃ እንለብሳለን፤ ከስር ውሃ መቀመቅ ውስጥ እንሰጥማለን…” (ገጽ 10)
ተጨማሪ ምሳሌ ቢያስፈልግም እነሆ፤
“7,000 የፈረስ ጉልበት የሚያመነጨው የጀልባዋ ሞተር እንደ አንዳች ያጓራል፡፡ ማዕበሉን ሰንጥቆ ለማለፍ የጀልባዋ መቅዘፊያዎች እንደ አንዳች ይሽከረከራሉ፡፡ ባህሩ ተበርግዶ እልም ያለ ገደል ይፈጥራል፡፡ ጀልባዋን ሙሉ በሙሉ ይውጣትና መልሶ ተጉመጥምጦ እንደተፋት ሁሉ ባህሩ ደረት ላይ ትገኛለች፡፡ ቀይ ባህር ካለው ጥልቀትና ስፋት አኳያ 118 ቶን የሚከብደው የጀልባዋ አካል የቡሽን ያህል አትከብደውም፡፡ ከማዶ እንደ ጥቀርሻ የጠቆረ የባህር አካል ተንደርድሮ መጥቶ ይላተመዋል። እሷም እንደ ሰይፍ ሰንጥቃው ወደፊት ትመነጨቃለች፡፡ አንዳች ዓይነት የቁጣ፥ የመዓት ድምጽ በድፍን ባህሩ ላይ ያስተጋባል” (ገጽ 104)
የመጽሐፉ ባለታሪኮች በርካታ ናቸው። በይበልጥ ጎልተው የሚታዩት ግን ከወንዶቹ መሐከል ያሬድ ሐጎስ፥ ስንታየሁ፥ በብዙ ቦታ ባናየውም ሊረሳ የማይቻለው ሌናተናንት አሸናፊ ዋቅጅራ (የጀልባ 202 አዛዥ)፤ ከሴቶች መሐከል ደሞ ገነት አስገዶም፥ ዓወት ግርማይ ፥ እና ኮማሪቷ አበባ አድማሱ ይገኙባቸዋል፡፡ እነዚህ የመጽሐፉ ባለታሪኮች በገሐዱ ዓለም የነበሩ ይሁኑ ወይ ደሞ የፈጠራ ገጸ ባህሪያት ይሁኑ አንባቢው ለይቶ ለማወቅ ከቶም አይቻለውም፡፡ ነገር ግን የፈጠራ ታሪክ ገጸ ባህሪያት ከሆኑ በገሐዱ ዓለም ሞዴል እንዳላቸው ሊያጠራጥር አይችልም፤ ታሪኩ በእውነተኛ ሁነት ላይ የተመሰረተ ነው ስለተባለ፡፡
ለመሆኑ የመጽሐፉ ዓላማ ምንድነው? የገጸ ባህርያቱን ስሞች ስናጤን እያንዳንዳቸው ከየት ብሔረሰብ እንደፈለቁ ይጠቁሙናል፡፡ ከሁለት የተለያዩ ብሔረሰቦች የተፈጠሩም አሉ። ነገር ግን ሁሉም ለማለት ይቻላል እንደ ውሁድ ኢትዮጵያውያን ይተያያሉ እንጂ የብሔረሰብ ማንነታቸውን ከቁም ነገር ሲያስገቡ አናይም፡፡ ትንሽ ያፈነገጠ አመለካከት ያላቸው ቢኖሩ ከሰሜን ጫፍ በኩል ያሉት ብቻ ናቸው፡፡
በትረካው መጨረሻ አካባቢ ሌፍተናንት አሸናፊ ወደ ሱማሌ ከመኮብለሉ በፊት የፈጸመው ድርጊት አንባቢውን ግራ ያጋባዋል፡፡ መርከበኞቹ ከመርከቡ ዘልለው ወርደው ባህር ውስጥ እንዲገቡ ያዝዛቸዋል። እነሱም በዋና ነፍሳቸውን ለማዳን ሲጥሩ ይታያሉ፡ የሞቱት ሞተው የተቀሩት ይተርፋሉ፡፡ ግን የሌተናንት አሸናፊ ድርጊት ምን ትርጉም አለው? እነዚህ መርከበኞች በእሱ ስር ሆነው የሚያገለግሉ ናቸው፡፡ በደል ሰርተውበት እንደሆነ የተነገረ ነገር የለም፡፡ ነገር ግን ለከፋ አደጋ አጋልጧቸው መኮብለሉ ትርጉሙ ምንድን ነው? ነገሩ እንቆቅልሽ ይሆንብናል፡፡
የእነዚህ መርከበኞች ዕጣ ፈንታ ይህ ብቻ ቢሆን ኖሮ ቢያሳዝንም “መቼስ ምን ይደረጋል!” ተብሎ ሊታለፍ ይችል ነበር፡፡ ነገር ግን በዚህ ጦስ ምክንያት ባልፈጸሙት ወንጀል ተከስሰው ለፍርድ ሲቀርቡ እናያለን፡፡ እነሱ የአዛዣቸው ሰለባ ከመሆን በስተቀር አንዳችም የፈጸሙት ወንጀል የለም፤ ያሬድ ሀጎስ ቀደም ብሎ ለመሰደድ ያደረገው ያልተሳካ ሙከራ እንዳለ ሆኖ፣ ታዲያ ለምንድነው ለፍርድ የቀረቡት? ምክንያቱን ለመረዳት አሁንም ከመጽሐፉ መጥቀስ ግድ ይላል፤
“የኢትዮጵያ አብዮተኞችም እንዲሁ ራሳቸውን ከወንጀል ለማጽዳት ባለፉት አስራ አምስት ዓመታት የቀጠለውን የጦስ ፍየል መስዋዕት የማድረግና ማርከሻውን መፈክር አሰምቶ የማለፍ ልምድ፤ ዛሬ የጦስ ፍየል አራጁ የነገ ተረኛ እየሆነ ሞትን በቅብብሎሽ አኖሩት፡፡ ይህ የጦስ ፍየል ከምድር ጦር ፥ ከአየር ኃይል ፥ ከባህር ኃይል ፥ ከሲቪሉ ሕብረተሰብ እየታደነ የአብዮታዊያኑን ጦስና ጥንቡሳስ ይዞ ይገደልና በሟች ሬሳ ላይ መፈክር ይሰማል፡፡ ዛሬም ያሬድና ጓደኞቹ ባልሰሩት ወንጀል እንደ ወንጀለኛ ታፍነው ደህንነት ቢሮ በመገኘታቸው የጦስ ፍየል ሊያደርጓቸው መወሰኑ ወለል ብሎ ታየው፡፡” (ገጽ 440)
ስለ አስራ ሰባቱ ዓመታት የጨለማ ዘመን በርካታ ልብ ወለዶችና ኢ - ልብ ወለድ መጻሕፍት ከዚህ ቀደም ተጽፈዋል፤ የበዓሉ ግርማ “ኦሮማይ”፥ የአማኑኤል ሐዲስ “አስተኳሹ”፥ የባቢሌ ቶላ “የትውልድ ዕልቂት” (አውግቸው ተረፈ እንደተረጎመው) እና ሌሎችንም ለመጥቀስ ይቻላል። “መልህቅ” ከእነዚህ አንዱ መሆኑ ነው፡፡ የአብዮቱ ዘመን ታሪክ በእነዚህ ብቻ ሊወሰን የሚችልም አይደለም፡፡ አሳታሚ በማጣት በየጠረጴዛው ኪስ ውስጥ ተዘግቶባቸው የሚኖሩ ልብ ወለዶችና ኢ - ልብወለድ መጻሕፍት እንዳሉ በቀላሉ መገመት ይቻላል፡፡ ከድርጊቶቹ አስከፊነት የተነሳ ዛሬ ብቻ ሳይሆን ወደፊት ከአምሳና መቶ አመታት በኋላም በታሪካዊ ልብ ወለድ መልክ ሌሎች በርካታ መጻሕፍት እንደሚዘጋጁ ለመገመት ነቢይ መሆን አያሻውም፡፡     

    ከየካቲት 9 ቀን 2010 ዓ.ም ጀምሮ ለሚቀጥሉት 6 ወራት በአገሪቱ ላይ የተጣለውን የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ ዓለም አቀፉ ማህበረሰብና የምዕራብ መንግስታት፣በጥርጣሬና በስጋት ነው የተቀበሉት፡፡ የአሜሪካ መንግስትና የአውሮፓ ህብረትም፤አስቸኳይ ጊዜ አዋጁን አስመልክቶ ያወጡት መግለጫ ከወትሮው የተለየ ነው፡፡  
አዋጁን በፅኑ የተቃወመው የአሜሪካ መንግስት በኤምባሲው በኩል ባወጣው መግለጫ፤ “የኢትዮጵያ መንግስት በተለይ በመሰብሰብና ሀሳብን በነፃነት በመግለጽ መብት ላይ ገደብ የሚጥለውን የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ ማወጁ፣ከቅርብ ጊዜ ወዲህ የተፈጠረውን ሁሉን አሳታፊ የሆነ የለውጥ መነሳሳት የሚያቀጭጭ፣ ይሰፋል ተብሎ በተስፋ የሚጠበቀውን የፖለቲካ ምህዳርም የበለጠ የሚያጠብ ነው” ብሏል፡፡   
 “የተፈጠሩት ሁከቶችና ብጥብጦች የሰው ህይወትን እየቀጠፉ እንደሆኑና በዚህም መንግስት ጭንቀት ውስጥ መግባቱን እንገነዘባለን” ያለው ኤምባሲው፤“ሆኖም ለዚህ አይነቱ ችግር መፍትሄው  መብትን መገደብ ሳይሆን የበለጠ ነፃነትን መፍቀድ ነው” ብሏል -የአስቸኳይ ጊዜ አዋጁን መውጣት አጥብቆ እንደሚቃወመው በመግለጽ፡፡
የአውሮፓ ህብረት በበኩሉ፤መንግስት የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ ማወጁ እየተካሄደ ያለውን የፖለቲካ ማሻሻያ በእጅጉ የሚጎዳ ነው ብሏል - በመግለጫው፡፡  
“አዋጁ መልካሙን ጅምር ሊያጠፋው ይችላል፤ከተቻለ የአጭር ጊዜያት ቆይታ ይኑረው” ሲልም ለመንግስት ምክር ለግሷል - ህብረቱ፡፡  
አዋጁ በሚተገበርባቸው ጊዜያት መሰረታዊ የሰብአዊ መብቶች እንዲከበሩና መሰረታዊ መብቶች እንዲረጋገጡ የአውሮፓ ህብረት የጠየቀ ሲሆን ለሀገሪቱ ሁነኛ የፖለቲካ መፍትሄ ሊሆን የሚችለው ከተቃዋሚዎችና ከሀገሪቱ የፖለቲካ ተዋናዮች ጋር የሚደረግ  ውይይት ነው ተብሏል፡፡
በኢትዮጵያ የኔዘርላንድ አምባሳደር ቤንት ቫን በሰጡት አስተያየት፤አዋጁ የሰብአዊ መብቶችን እንዳይገድብ ስጋት አለን ብለዋል፡፡ የአዋጁ የቆይታ ጊዜ ማጠር የሚችልበት ሁኔታም መመቻቸት እንዳለበት ጠቁመዋል፡፡
“ጠቅላይ ሚኒስትሩ ስልጣን ለመልቀቅ መወሰናቸው በበጎ የሚታይ ቢሆንም የአስቸኳይ ጊዜ አዋጁ የዜጎችን የመናገር፣ የመሰብሰብና ሃሳብን የመግለፅ መብቶች የሚገድብ በመሆኑ ያሳስበኛል” ያለው ደግሞ የእንግሊዝ መንግስት ነው፡፡  
አዋጁ ለአጭር ጊዜ ብቻ ይተገበራል የሚል ተስፋ አለኝ ያለው የእንግሊዝ መንግስት፤ “በዚህ ጊዜ ውስጥም ቢሆን መንግስት መሰረታዊ የዜጎችን ሰብአዊ መብቶች ያከብራል የሚል እምነት አለን” ብሏል፡፡ “በአስቸኳይ ጊዜ አዋጁ ወቅትም ሰዎችን በጅምላ ማሰርና ኢንተርኔትን ማቋረጥ ሊተገበር አይገባም” ሲል አሳስቧል - የእንግሊዝ መንግስት የአፍሪካ ጉዳዮች ሚኒስቴር ባወጣው መግለጫ፡፡
“የኢትዮጵያ መንግስት ሰላማዊ፣ ፈጣንና ግልፅነት በተሞላው መንገድ የለውጥ ሂደቱን ለማስቀጠል አዲሱን ጠቅላይ ሚኒስትር ይመርጣል ብለን ተስፋ እናደርጋለን” ያለው መግለጫው፤ “ስለ ወዳጅነታችንም ለኢትዮጵያውያን እርዳታችን አይለይም” ብሏል፡፡
በሌላ በኩል ከተለያዩ የዓለም ሀገራት አምባሳደሮች ጋር በአስቸኳይ ጊዜ አዋጁ ላይ ሰሞኑን ውይይት ያደረጉት የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሩ ዶ/ር ወርቅነህ ገበየሁ፤”አዋጁ ሀገሪቱ የገጠማትን የሰላምና መረጋጋት ችግር ለመፍታት የተዘጋጀ ነው፣ ተግባራዊ ከተደረገ ወዲህም የሀገሪቱ ሁኔታ መሻሻል አሳይቷል” በማለት የአዋጁን ጠቀሜታ ለዲፕሎማቶቹ አስረድተዋል፡፡