Administrator

Administrator

በአስቸኳይ ጊዜ አዋጁ ወቅት ከ390 ሺ በላይ ሚሊሻዎች ሰልጥነዋል
ከ7ሺ በላይ ተጠርጣሪዎች ክሳቸውን እየተከታተሉ ነው
የሦስት ሚኒስትሮች ሹመት ፀድቋል

ከመስከረም 28 ቀን 2009 ዓ.ም ጀምሮ ለ11 ወራት በሥራ ላይ የቆየው የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ  በትላንትናው ዕለት ተነሳ፡፡
የህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ትናንት የአስቸኳይ ጊዜ አዋጁ እንዲነሳ የቀረበውን የውሳኔ ሃሳብ ያፀደቀ ሲሆን ባካሄደው አንደኛው አስቸኳይ ስብሰባ ላይ በቀረበው ሪፖርት መሰረት፤ የአስቸኳይ ጊዜ አዋጁ ከታወጀበት መስከረም 28 ጀምሮ በኦሮሚያ 233 ሺ 070፣ በአማራ 143 ሺ 459 እንዲሁም በደቡብ 16 ሺ 475 ሚሊሺያዎች መሰልጠናቸው ተገልጿል። በተጨማሪም በየክልሉ ያሉ የብሔራዊ ተጠባባቂ የሰራዊት አባላትን የማጠናከር ሥራ ተሰርቷል ተብሏል፡፡
የተፈጠረውን አለመረጋጋት ለማስቆምና የህግ የበላይነትን ለማረጋገጥ የሚያስችሉ ሥራዎችን በተመለከተም በሁከትና ብጥብጡ ተሳትፈዋል የተባሉ ከኦሮሚያ ክልል 4136፣ ከአማራ ክልል 1888፣ ከደቡብ ክልል 1166፣ ከአዲስ አበባ 547 በድምሩ 7737 ተጠርጣሪዎች በተለያየ ደረጃ ባሉ ፍርድ ቤቶች ክሳቸውን እየተከታተሉ መሆኑ ተጠቁሟል፡፡ ከ21 ሺ በላይ ተጠርጣሪዎችም በሁለት ዙር የተሃድሶ ስልጠና ወስደው፣ ወደ ህብረተሰቡ እንዲቀላቀሉ መደረጉ በሪፖርቱ ላይ ተመልክቷል። ኮማንድ ፖስቱ የታጠቁ አሸባሪዎችንና ፀረ-ሰላም ሃይሎችን ለመቆጣጠር የተሰሩ ሥራዎች ብሎ ባቀረበው ሪፖርት ላይ እንደተገለፀው፤ በኦሮሚያ 325፣ በአማራ 275፣ በደቡብ 109 በድምሩ 709 ሸማቂዎችና የታጠቁ ኃይሎች፣ ከህዝብና ከመስተዳደር አካላት ጋር በመሆን ለመቆጣጠር እንደተቻለ ጠቁሟል፡፡ ህገወጥ የመሣሪያ ዝውውርን ለመቆጣጠር ከ97 በላይ አዳዲስ ኬላዎችን በማቋቋምና 196 ነባር ኬላዎችን በማጠናከር የተለያዩ የነፍስ ወከፍና የቡድን ጦር መሳሪያዎችን በቁጥጥር ሥር ማዋሉንም አስታውቋል፡፡ ከነበረው ሁኔታ ልምድ በመውሰድ የጦር መሣሪያ አያያዝና አጠቃቀም ላይ ረቂቅ አዋጅ እየተዘጋጀ መሆኑንና አዋጁ በሥራ ላይ ሲውል የዚህ አይነት ችግሮችን ለመፍታት ከፍተኛ አስተዋፅኦ እንደሚኖረውም ተጠቁሟል፡፡
በቅርቡ ከግብር ክፍያ ጋር በተያያዘ ተከስቶ የነበረውን የፀጥታ ችግር የየክልሉ የፀጥታ አካላት በራሣቸው አቅም መፍታት መቻላቸው፣ የኮማንድ ፖስቱ አስፈላጊነት ወሣኝ አለመሆኑን አመላክቷል ያለው ሪፖርቱ፤ የፌደራል የፀጥታ አካላትና የክልል የፀጥታ አካላት በአስቸኳይ ጊዜ አዋጁ ወቅት ያዳበሩትን በጋራ ተቀናጅቶ የመስራት ልምድ በመጠቀም ችግሮችን ለመፍታት እንደሚቻል ጠቁሟል፡፡ ኮማንድ ፖስቱ ሲያከናውን የቆያቸውን ሥራዎች ደረጃ በደረጃ በአካባቢው ላሉ የፀጥታና የሚመለከታቸው አካላት እያስረከበ፣ የቅርብ ድጋፍ ሲያደርግ መቆየቱም ተገልጿል፡፡
በየቦታው እያጋጠሙ ያሉ ጥቃቅን ክስተቶችና ያልተቋጩ መለስተኛ ሥራዎች ቢኖሩም እነዚህ ሥራዎች በመደበኛ ሁኔታ፣ በየደረጃው ካሉ የፀጥታና የመስተዳድር አካላት አቅም በላይ ሊሆኑ ስለማይችሉ የአስቸኳይ ጊዜ አዋጁ እንዲነሳና ቀሪ ሥራዎች በመደበኛው የህግ አግባብ እንዲፈፀሙ ለምክር ቤቱ የውሣኔ ሀሳብ ቀርቧል፡፡ ምክር ቤቱ የአስቸኳይ ጊዜ አዋጁ በመነሣቱ ጉዳይ ላይ ድምፅ መስጠት የሚጠበቅበት ባለመሆኑ፣ የምክር ቤቱ አባላት ድምፅ ሣያስፈልግ የአስቸኳይ ጊዜ አዋጁ ከትላንት ሐምሌ 28 ቀን ጀምሮ መነሣቱ ተገልጿል፡፡  
በሌላ በኩል በትላንትናው ዕለት ለአስቸኳይ ስብሰባ የተጠራው ምክር ቤቱ፤ የ3 ሚኒስትሮችን ሹመትም አፅድቋል፡፡ በዚህም መሰረት ባለፈው ህዳር ወር የኢትዮጵያ ገቢዎችና ጉምሩክ ባለስልጣን ዋና ዳይሬክተር ሆነው የተሾሙት አቶ ከበደ ጫኔ፤ የፌደራል አርብቶ አደር ልማት ጉዳዮች ሚኒስትር፣ በትምህርት ሚኒስቴር የአጠቃላይ ትምህርት ዘርፍ ሚኒስቴር ዴኤታ የነበሩት ዶ/ር ጥላዬ ጌቴ፣ የትምህርት ሚኒስትር እንዲሁም የኢትዮጵያ ገቢዎች ጉምሩክ ባለስልጣን የጉምሩክ ዘርፍ ምክትል ዋና ዳይሬክተር የነበሩት አቶ ሞገስ ባልቻ፣ በሚኒስትር ማዕረግ ዋና ዳይሬክተር ሆነው ተሹመዋል፡፡  


   • በአዳዲስ አቅጣጫዎች መጠናከሩን ቀጥሏል
                    • ከ10 በላይ ጋዜጠኞች ለዓለም ሻምፒዮናው ለንደን ይጓዛሉ
                    • አዲስ ድረገፅ ያስመርቃል
                    • የክልል ጋዜጠኞችን በሚያሳትፍ መዋቅር የመስራት እቅድ አለው

      የኢትዮጵያ ስፖርት ጋዜጠኞች ማህበር በአዳዲስ የስራ አቅጣጫዎች ተጠናክሮ እንደሚቀጥል ፕሬዝዳንቱ አቶ ዮናስ ተሾመ ለስፖርት አድማስ ገለፁ፡፡ ማህበሩ ከዓለም አቀፍ የስፖርት ማህበራት ጋር የላቀ ግንኙነት ፈጥሮ በመስራት አባላቱን ተጠቃሚ እያደረገ ነው ብሏል። በአዲስ መልክ ተደራጅቶ ከተቋቋመ ሁለተኛ የስራ ዘመኑን የያዘው ማህበሩ በዛሬው እለት ከአትሌቲክስ ፌደሬሽን አብይ ስፖንሰር ‹‹ሶፊማልት›› ባገኘው ድጋፍ ለሁሉም የስፖርት ጋዜጠኞች በ16ኛው የዓለም አትሌቲክስ ሻምፒዮና ላይ ያተኮረ ስልጠና አዘጋጅቷል፡፡ በስልጠናው ላይ የኢትዮያ አትሌቲክስ ፌደሬሽን ፕሬዝዳንት ኃይሌ ገብረስላሴ እንዲሁም የሶፊ ማልት እና የሄኒከን ብራንድ ማናጀር ራህዋ ገብረመስቀል በክብር እንግድነት ይገኛሉ፡፡ ስልጠናውን የሚሰጠው እውቅ የአትሌቲክስ ጋዜጠኛ፤ የአይኤኤኤፍ ዘጋቢ እና የማህበሩ አባል ኤልሻዳይ ነጋሽ ነው፡፡ በስልጠናው የዓለም ሻምፒዮናውን የሚመለከቱ ወቅታዊ መረጃዎች፤ የዘገባ ሁኔታዎችና አሰራሮችን በጥልቀት ይዳሰሳሉ፡፡ ኃይሌ ገብረስላሴ አጋጣሚውን በመጠቀም ለስፖርት ጋዜጠኞች ልዩ መልዕክት እንደሚያስተላልፍ የሚጠበቅ ሲሆን፤ የስፖርት ጋዜጠኞች ማህበር ኦፊሴላዊ ድረገፁንም እንደሚያስመርቅ ታውቋል፡፡ በሌላ በኩል ለንደን የምታዘጋጀውን 16ኛው የዓለም አትሌቲክስ ሻምፒዮና በተለያዩ የሚዲያ አውታሮች ለመዘገብ ከ10 በላይ የማህበሩ አባላት  እንደሚጓዙ ለስፖርት አድማስ የጠቀሰው ፕሬዝዳንቱ አቶ ዮናስ፤  ስራ አስፈፃሚው በሁለተኛው የስራ ዘመን የመጀመርያው አንድ ዓመት ውስጥ በርካታ ጋዜጠኞችን ዓለም አቀፋዊ እና አህጉራዊ ውድድሮችን እንዲዘግቡ እድሉን በመፍጠር በትጋት መስራቱን በተለይ ደግሞ የ4 ጋዜጠኞችን ሙሉ ወጭ በመሸፈን ድጋፍ መስጠቱን አመልክቷል፡፡
በሁለተኛው የስራ ዘመን ላይ የሚገኘው የማህበሩ ስራ አስፈፃሚ  በመጀመርያው የስራ ዘመን የነበሩ የኮሚቴ አባላቱን ይዞ በመቀጠል ሁለት አዳዲስ አባላት ተጨምረውበት ለተጨማሪ አራት አመታት እንዲቀጥል የተወሰነው ከዓመት በፊት ነበር፡፡ ስለሆነም የማህበሩ ፕሬዝዳንት ዮናስ ተሾመ፣ ፀሀፊ መንሱር አብዱልቀኒ፣ ደረጃ ጠገናው፤ የማህበሩ ገንዘብ ያዥ ቆንጂት ተሾመ ውጪ ፍቅር ይልቃል፣ ሀና ገ/ስላሴ፣ አርአያት ራያ፣ ግርማቸው ከበደ፣ ታደለ አሰፋ፣ ዳግም ዝናቡ፣ ኃይለእግዚአብሔር አድሃኖም በስራ አስፈፃሚነት ኮሚቴ እያገለገሉ ናቸው፡፡ የስራ አስፈፃሚ አባላቱ በ4 ንዑስ ኮሚቴዎች እና ሁለት ኮሚሽኖች በመከፋፈል እየሰሩም ይገኛል፡፡
የኢትዮጵያ የስፖርት ጋዜጠኞች ማህበር የሙያተኛውን አቅም ለማጎልበት ትኩረት ማድረጉን የገለፀው ፕሬዝዳንቱ በየዓመቱ ከ4 በላይ ስልጠናዎችን ለማዘጋጀት እቅድ መያዙን ስልጠናዎቹን በአዲስ አበባ እና በክልል ከተሞች ለመስጠት እንደሚፈልግና በተለይ በክልል የሚሰሩ የስፖርት ጋዜጠኞችን በሚያሳትፉ እንቅስቃሴዎች ይሰራል ብሏል፡፡
በየዓመቱ ከዓለም ዓቀፉ የአትሌቲክስ ፌዴሬሽኖች ማህበር (IAAF) የሚገኙ ዕድሎች  በፍትሃዊነት ለሁሉም መገናኛ ብዙሃን ለማዳረስ ጥረት እናደርጋለን ያለው አቶ ዮናስ፤  ባለፈው 1 ዓመት በተለያዩ ዓለም አቀፋዊ እና አህጉራዊ ውድድሮች ለዘገባ የተላኩ ጋዜጠኞች በየሚዲያ አውታሮቻቸው ከበፊቱ በተሻለ የሰጧቸው የዘገባ ሽፋኖች እንደሚያበረታቱ ገልጿል፡፡
በዓለም ዓቀፍ የስፖርት ማህበራት  የሚኖረውን እውቅናና የተቀባይነት ደረጃ ለማሳደግ ከዓለም አቀፉ የአትሌቲክስ ፌደሬሽኖች ማህበር እና ከዓለም አቀፉ የስፖርት ጋዜጠኞች ማህበር ያለው ግንኙነት እየጠናከረ መጥቷል፡፡ በኢትዮጵያ የሚከናወኑ የስፖርት እንቅስቃሴዎችና ዓለም አቀፍ ትኩረት ሊያገኙ የሚገባቸው የዜና እና የዘገባ ሽፋኖች እየበዙ ናቸው፡፡ በአገር ውስጥ ከሚገኙ የስፖርቱ ባለድርሻ አካላት እና አጋሮች ጋር በተለያዩ ርእሰ ጉዳዮች በስፋት ለመንቀሳቀስ እየሞከረ ነው፡፡ በተለይ ከኦሎምፒክ ኮሚቴው፤ ከአትሌቲክስ እና ከእግር ኳስ ፌደሬሽኖች ጋር ነው፡፡
የማህበሩ አደረጃጀት የዓለም አቀፉን የስፖርት ጋዜጠኞች ማህበር ስርዓት እንዲከተል እንፈልጋለን በማለት ለስፖርት አድማስ የተናገረው ፕሬዝዳንቱ አቶ ዮናስ ተሾመ፤ በሚቀጥሉት ሁለት ዓመታት በአፍሪካ የስፖርት ጋዜጠኞች ማህበር ያለውን ተፅእኖ ፈጣሪነት በማሳደግ አህጉራዊውን ጉባኤ ለማስተናገድ ማቀዱን ጠቁሟል፡፡ ከሁለት ዓመታት በፊት በታላቁ ሩጫ በኢትዮጵያ አማካኝነት አዲስ አበባ ላይ የዓለም አቀፉ የስፖርት ጋዜጠኞች ማህበር ስራ አስፈፃሚ ልዩ ስብሰባ በአዲስ አበባ መስተናገዱ ይታወሳል፡፡  
የኢትዮጵያ የስፖርት ጋዜጠኞች ማህበር በአሁኑ ወቅት ከ100 በላይ አባላት ያሉት ሲሆን፤ ከነዚህ መካከል 85ቱ ዓለም ዓቀፍ የስፖርት ጋዜጠኞች ማህበር አባል ናቸው፡፡

  ይድረስ ለላንቺና ላንተ አምድ አዘጋጆች ከነታዳሚዎቻችሁ እንደምንሰነበታችሁ የሚለውን ሰላምታ ያገኘነው ከአንድ አንባቢ ነው፡፡ የግል ታሪኩን የብዙዎች ሰዎች ገጠመኝ ሊሆን ስለሚችል እባካችሁ አስነብቡልኝ ብሎናል፡፡ የአምዱ ዝግጅት ክፍልም በሀሳቡ በመስማማት እነሆ ለንባብ ብሎአል፡፡
እኔ ያደግሁት በጣም ብዙ ቤተሰብ ውስጥ ነው፡፡ እናትና አባቴ አስር ልጆች ነበር የወለዱት፡፡ እኔ አራተኛ ስሆን ወንድ ለመወለዱ ግን የመጀመሪያ ነበርኩ። የእኔ ታላላቆች ሴቶች ናቸው፡፡ የሚገርመው ነገር ከእኔም በሁዋላ ወንድ አልተወለደም፡፡ ስለዚህም ስሜ የወንድወሰን ተባለ፡፡ እናትና አባቴ ሁልጊዜ የሚናገሩት ነገር ነበረ፡፡ ይኼውም እኔ ወንድ ልጅ ስለሆንኩ ከመንደር ልጆች ጋር ኳስ ስጫወት እውላለሁ፡፡ ወደእኔ ቤት ይመጣሉ ወደእነሱ ቤት እሄዳለሁ፡፡ ታዲያ እናቴ ምርር ሲላት “ምን የመንደር ውሪ ተሰበስባለህ? እዚህ ያለው ሰው መች አነሰና ነው? አርፈህ አትቀመጥም? የሁልጊዜ ንግግርዋ ነበር፡፡ እኔ ግን ልጅ በጣም እወድ ስለነበር ብቻዬን መሆን አልፈልግም ነበር፡፡ አባቴ ደግሞ በበኩሉ “እኔ በበኩሌ የምፈራው ይህ ልጅ ካለዘር እንዳይቀር ነው” ይል ነበር፡፡ በዚህ ንግግሩ እንዲያውም እናትና አባቴ ሁልጊዜ ነበር የሚጣሉት፡፡
ትዳር መያዝ አይቀርምና ጊዜው ደርሶ ተዳርኩኝ፡፡ ነገር ግን አመታት እየተቆጠሩ ሄዱ፡፡ ልጅ አልመጣም። አባቴም “ይኼውላችሁዋ… እኔ የሚሰማኝ አላገኘሁም እንጂ ብዬ ነበር” ሲል እናቴ ደግሞ “ብዬ ነበር ማለት ምን ማለት ነው? ልጅ በሰው እጅ አይሰራ…ምን ማድረግ ይቻል ነበር? መካንነቱ ከእሱ ቢሆንስ?” አባቴም “ተይ ባክሽ ይቺ… ምን ትላለች… እኔ እንደሆንኩ በዘሬም መካን የለም…. በእርግጥ ያንቺን አላውቅም…” እናቴም ትመልስና “ወገኛ ነህ እባክህ፡፡ ስለእኔ እንኩዋን አሳምረህ ታውቃለህ፡፡ በልጅቱም በኩል የሆነ እንደሆነ ዘር ማንዘርዋን አሳምረን እናውቀዋለን፡፡ ወላዶች ናቸው። የራስ ልጅ ቢሆንስ መካን የሆነው? ምን ልትል ነው? ትለዋለች፡፡
የእናትና የአባቴ ንትርክ ጠዋት ማታ መሆኑን ታናናሽ እህቶቼ ይነግሩኛል፡፡ እኔ ያስጨነቀኝ ግን የእነሱ ጉዳይ አልነበረም፡፡ የእራሴ የትዳር መቀጠልና አለመቀጠል … እንዲሁም የልጅቱም ሆነ የእኔ ቤተሰቦች ፍላጎት መሟላት አለመቻሉ ነበር፡፡ ነገር ግን በቃ… አልኩና ቆርጬ ተነሳሁ፡፡ ይህ ነገር ስንፍና አይፈልግም ብዬ ከሐኪሞች ጋር መመካከር ጀመርኩኝ፡፡ ወደ ሕክምናው የሄድነው በተጋባን በ5 አመታችን ነበር። በጊዜው እኔ ማለትም ወንድየው ወደ 40 አመት የገባሁ ስሆን ባለቤቴ ደግሞ በሰላሳዎቹ መጀመሪያ ላይ ነበረች። በእርግጥ በእነዚህ የትዳራችን 5 አመታት ለማርገዝ አስበን ባይሆንም እራሳችንን ግን አላቀብንም። ምክንያቱ ምንድነው? የሚለውን መልስ ለማግኘት ወደ ሐኪም ስንቀርብ ግን ዶክተራችን ጥሩ የጤና ሁኔታ ላይ እንደምንገኝ እና በትእግስት እንድንቆይ  ነግሮናል፡፡ ታዲያ ብንጠብቅ ብንጠብቅ  እርግዝናው በፍጹም እውን ሊሆን አልቻለም፡፡ ብዙ ሞከርን፡፡ ግን አልተሳካም፡፡ በጣም በንዴት ለዶክተሩ እንዲህ አልኩት፡፡ “እኔ ገና የ40 አመት ሰው ነኝ፡፡ ሚስቴ ደግሞ የ32 አመት ሴት ናት፡፡ ምን ምክንያት ቢገኝ ነው የማታረግዘው?” ብዬ ጠየቅሁት፡፡ የእሱም መልስ አሁንም ጤነኛ ናችሁ ሞክሩ የሚል ሆነ። እኛ በጉጉት በራሳችን መንገድ አላማችንን ለማሳካት ጥረታችንን ጀመርን፡፡ ስንጀምረው ሁለታችንም ቶሎ እንደሚሆን አምነን ነበር። ምክንያቱም ሁለታችንም እንዋደዳለን፡፡ ባለቤቴም የእርግዝና መከላከያ ሞክራ እንኩዋን አታውቅም፡፡ እንዲያውም የወርአበባ ማስተካከያ እየተባለ ለማርገዝ ስንፈልግ በሞከርነው ሕክምና ኪኒኑን የዋጠችበት ወቅት ነበር፡፡ ምንም ቢደረግ ግን የወር አበባዋ  አይቀርም…. እርግዝና የለም። እናም ግራ ገባን፡፡ ትክከለኛው ጊዜ ሲደርስ ሊሆን እንደሚችል ለራሳችን ነግረን ጥረታችንን ኮስተር ብለን በቅንነት ቀጠልን፡፡ በኋላ ላይ ነበር ልጅ ለመውለድ የምናደርገውን ጥረት የሚያውክ ነገር በሁለታችንም መካከል መኖሩን ያመንኩት፡፡ እንዴት አወቅህ ብትሉኝ ስለጉዳዩ ማንበብ በመጀመሬ ነው፡፡ ሰዎች ልጅ መውለድ አልቻሉም ወይንም የማይችሉ ናቸው የሚባለው ካለምንም ጥንቃቄ ለአመታት ወሲብ እየፈጸሙ ነገር ግን ልጀ መውለድ ካልቻሉ እና ወይንም ቀደም ሲል የተወሰነ ልጅ ወልደው ነገር ግን ሴትዋ ድጋሚ ማርገዝ ሲያቅታት ነው፡፡ ይላል፡፡ እኛ ግን ከመጀመሪያውኑም ስላልወለድን ምክንያቱን ለማወቅ አሁንም የቻልኩትን ያህል ማንበብ ጀመርኩኝ፡፡ በዚህ ዙሪያ የተጻፉት መጽሐፎች ብዙ ነገር ይመክራሉ፡፡ ለምሳሌም፡-
የሴትዋ እድሜ በተለይም በተቻለ መጠን 29 አመት እስኪሆን ባለው ጊዜ ማርገዝ ብትችል፣
በተለያዩ ሕመሞች ምክንያት የተለያዩ መድሀኒቶችን መውሰድ፣
በወንድ ተፈጥሮአዊ ሁኔታ እና እንዲሁም በሴትዋ ተፈጥሮአዊ ሁኔታዎች ማለትም በስነተዋልዶ አካላት ላይ ሊፈጠሩ በሚችሉ ችግሮች፣
በአኑዋኑዋር ምክንያት ሰውነት ላይ ሊፈጠሩ የሚችሉ አንዳንድ ጫናዎች ማለትም፡-
ቅጥ ያጣ ውፍረት፣
መጠጥ መጠጣት፣
አንዳንድ እንደ ሲጋራ ማጤስ የመሳሰሉ አጉዋጉል ባህሪዮች፣
የአመጋገብ ሁኔታ፣‘
በቂ የሆነ የሰውነት እንቅስቃሴ አለማድረግ የመሳሰሉት ነገሮች ልጅ ለማግኘት የሚደረገውን ጥረት ሊያውክ እንደሚችል ተረዳሁ፡፡
ከዚህም በመነሳት ለባለቤቴ የሚከተሉትን ጥያቄዎች ለየራሳችን አናቅርብ አልኩዋት፡፡ ጥያቄዎቹም የሚከተሉት ነበሩ፡፡ ምንም የጤና እክል ከሌለብን እንዴት እነዚህ ልጅ መውለድ አልቻልንም? ምንድን ነበረ ማስተካከል የሚገባን? ሰውነታችንን በትክክል ባለመጠበቃችን ነው?  ወይንስ አልኮል በመጠጣታችን ጫት በመቃማችን? እያልን ለእራሳችን ጥያቄውን ለየብቻችን መልሰን ከዚያም በጋራ እንድንነጋገር ተስማማን፡፡ መልሱ ሲመጣ ግን የሁለታችንም ሀሳብ አንድ አይነት ነበር፡፡ ሁለታችንም… ልጅ የለን …ለማን ብለን ነው? እረ ብዪ …አረ ብላ… አረ ጠጪ… አረ ጠጣ…እየተባባልን በጣም እንበላለን… በጣም እንጠጣለን፡፡ ከዚያም በሁዋላ ቅዳሜና እሁድ ከጫት የሚለየን ማንም የለም፡፡ አንዳንድ ማህበራዊ ጉዳዮች ሲገጥሙን እንኩዋን ምክንያት እየሰጠን የምንቀርባቸው ጊዜያት በጣም ብዙ ናቸው፡፡ ይህ ልጅ ላለመውለድ ብቻም ሳይሆን ለራሳችንም ጤንነት ስህተትና ሊታረም የሚገባው መሆኑን አመንን፡፡
አንድ ቀን ሳንደባበቅ እንድንነጋገር ተስማማን። ከአዲስ አበባ ወጣ ብለን ማለትም ወደ ናዝሬት በመሔድ ለሁለት ቀን ቆየን፡፡ በዚያ መዝናኛ እያለን እስቲ የየሆዳችንን እንነጋገር ተባባልን፡፡ እውነታው እንደሚከተለው ነበር፡፡ እኔ ባልየው በተለይ በጣም ነበር የምበሳጨው፡፡ አባቴ እንደተናገረው መሐን ሆኜ መቅረቴ ነው…ወይኔ? እያልኩ ባለቤቴ ሳታየኝ እጅግ በጣም እበሳጭ ነበር፡፡ የሁዋላ ሁዋ ላም ባለቤቴን ሳናግራት…እኔ እኮ በየምሽቱ ከፈጣሪ ጋር እነጋገር ነበር፡፡ … ምን በድዬህ ነው ፈጣሪዬ? አረባክህ ከሰው አስተካክለኝ? እያልኩ እጅግ በጣም ነው የምጨነቀው፡፡ እንዲያውም ወሲብ ወደመፈጸም ስናመራ ለእራሴ…ምን ያደርግልኛል …ልጅ እንደሆነ አልወልድ…እያልኩ አማርራለሁ…ነበር ያለችኝ፡፡  
በሁኔታው እጅግ ተገርሜ እና አዝኜ ነበር ብድግ ብዬ ያቀፍኩዋት፡፡ ከዚህ በሁዋላ ለእኔ አንቺ እንደ ልጄ ነሽ የምቆጥርሽ … በቃ እርም ያድርግብኝ… ሁለተኛ ስለዚህ ነገር ብናስብ እግዚአብሔር ይፍረድብን አልኩዋት፡፡ እሱዋም እኔ ላንተ እያዘንኩ ነው እንጂ የምሰቃየው የምወድህ ባሌ ወንድሜ ስለሆንክ አንተን ካልከፋህ አረ እኔ ሁለተኛ ስለዚህ ነገር አላስብም አለችኝ፡፡ በዚህ ጊዜ ከተጋባን ወደ ስምንት አመት ሆኖናል፡፡ ሁለታችንም ስለወደፊቱ አኑዋኑዋራችንን ለእራሳችን ስንል ሁኔታዎችን እናስተካክል በሚለው ተስማምተን …አንዳንችን ለአንዳችን ቃል ገብተን በሙሉ ልብ በፍቅር ካለጭንቀት እንደ አዲስ ፍቅረኛ ተቃቅፈን አደርን፡፡ ወደቤታችንም ስንመለስ ያንኑ ቀጠልን፡፡ አዲስ ሕይወት ጀመርን፡፡  ልብ በሉ ብቻ፡፡ ይህ በሆነ በሶስተኛ ወሩ የወር አበባዋ ቀረ፡፡ አረ ተይው …አረ ተወው… እያሾፈብን ነው፡፡ ይልቅስ ሕመም እንዳይመጣ ታከሚ አልኩዋት፡፡ በሁለተኛውም ወር አልመጣም፡፡ ሕመም እንዳይሆን ፈርቼ ወደሕክምና ብወስዳት የምርመራው ውጤት እርግዝና ነው ተባለ፡፡ እኔና ባለቤቴ ተገርመን አሁንም ተነጋገርን፡፡ ከሆነ ይሁን ካልሆነም የራሱ ጉዳይ ብለን እራሳችንን ቅጥ ካጣ ደስታ ገደብን፡፡ ነገር ግን ሐኪማችንም እንደመሰከረው በመነጋገርና ጭንቀትን በማስወገድ ብቻ…እነሆ ዛሬ የሶስት ልጆች እናት እና አባት ነን፡፡ የመጀመሪያዋ ልጃችን ዘንድሮ ስምንተኛ ክፍልን ተፈተነች፡፡ ስለዚህ ኑሮን በአቅም ከማስተካከል …ባህርይን ከማረቅ ጀምሮ ወለድኩ አልወለድኩ ብሎ አለመጨነቅ ልጅ ለማግኘት ይረዳል፡፡

  ውሻውን በናይጀሪያው ፕሬዚዳንት ሙሃመድ ቡሃሪ ስም በመሰየሙ ባለፈው አመት የታሰረውና ሰላም የሚያደፈርስ ተግባር ፈጽሟል በሚል ክስ የተመሰረተበትን ናይጀሪያዊው ጆአኪም ኢሮኮን ጉዳይ ሲመረምር የቆየው ፍርድ ቤት፣ ግለሰቡን ከጥፋተኝነት ነጻ የሚያደርግ ውሳኔ አስተላልፏል፡፡
የፍርድ ቤቱ ዋና ዳኛ፤ ግለሰቡ የአገሪቱን ሰላም የሚያደፈርስ ተግባር ስለመፈጸሙ የሚያረጋግጥ በቂ ማስረጃ ባለመቅረቡ ተጠያቂ ሊሆን አይችልም በማለት ባለፈው ረቡዕ ነጻ መሆኑን የሚያረጋግጠውን ውሳኔ እንዳስተላለፉ ቢቢሲ ዘግቧል፡፡
ግለሰቡ ውሻውን በፕሬዚዳንቱ ስም መሰየሙን ለፖሊስ የጠቆመውና ያሳሰረው አንድ ጎረቤቱ የሆነ ሰው እንደነበር ያስታወሰው ዘገባው፤ እስራቱ  በመላ አገሪቱ ተቃውሞ ገጥሞት እንደነበርም ዘገባው አውስቷል፡፡
በአነስተኛ የንግድ ስራ ላይ ተሰማርቶ ህይወቱን የሚገፋው የ41 አመቱ ተከሳሽ፣ በውሻው ግራና ቀኝ ጎን ላይ ቡሃሪ የሚል ጽሁፍ በመለጠፍ፣ የፕሬዚዳንቱ ደጋፊዎች በሚበዙበት አካባቢ ሲንቀሳቀስ ታይቷል፤ ይህም ድርጊት ጸብ አጫሪና ሰላምን የሚያደፈርስ ነው በማለት ፖሊስ በቁጥጥር ስር አውሎ ክስ እንደመሰረተበትም ዘገባው አስታውሷል፡፡
ፍርድ ቤቱ ውሳኔውን ማስተላለፉን ተከትሎ፣ ግለሰቡ በሰጠው መግለጫ፣ “የምወደውን ውሻዬን በማደንቀው ጀግናዬ በፕሬዚዳንት ቡሃሪ ስም መሰየሜ ከመልካም ስሜት የመነጨ ነው፤ መታሰሬ አግባብ እንዳልነበር አውቃለሁ፣ ድርጊቱን በመቃወም ከጎኔ የቆማችሁትን ሁሉ አመሰግናለሁ” ማለቱንም ዘገባው ገልጧል፡፡

    ደመወዝ የሚቀበሉት ህግ አስገድዷቸው ነው

       የአሜሪካው ፕሬዚዳንት ዶናልድ ትራምፕ፤ 100 ሺህ ዶላር የሚሆነውን የ2017 የሁለተኛው ሩብ አመት ደመወዛቸውን፣ አሜሪካውያን ተማሪዎች ከፍተኛ ጥራት ያለው ትምህርት እንዲያገኙ ለመርዳት፣ለአገሪቱ የትምህርት ሚኒስቴር በስጦታ መልክ መለገሳቸው ተዘግቧል፡፡
ትራምፕ ባለፈው ረቡዕ በዋይት ሃውስ የፕሬስ ጸሃፊ ሳራ ሳንደርስ በኩል ለትምህርት ሚኒስቴር በስጦታ የለገሱት ገንዘብ በሳይንስ፣ ቴክኖሎጂ፣ ምህንድስናና በመሳሰሉት የትምህርት መስኮች ዝንባሌ ያላቸው የአገሪቱ ህጻናት ጥራት ያለው ትምህርት እንዲያገኙ ለማገዝ እንደሚውል ዋሽንግተን ፖስት ዘግቧል፡፡
የትምህርት ጸሃፊዋ ቤትሲ ዴቮስ ስጦታውን ከተቀበሉ በኋላ በሰጡት መግለጫ፣ ልገሳው ትራምፕ ሁሉም የአገሪቱ ህጻናት ጥራቱን የጠበቀ ትምህርት እንዲያገኙ ለማስቻልና የትምህርት ስርዓቱን ለመደገፍ ያላቸውን ቁርጠኛ አቋም ያሳዩበት ነው ማለታቸውንም ዘገባው አመልክቷል፡፡
ትራምፕ ባለፈው ሩብ አመት በተመሳሳይ ሁኔታ ደመወዛቸውን በመለገስ ሁለት ፕሮጀክቶችን መደገፋቸውን ያስታወሰው ዘገባው፤ ቀዳማዊት እመቤት ኢቫንካ ትራምፕም አሜሪካውያን ልጃገረድ ተማሪዎች፣ የንባብ ልምዳቸውን እንዲያዳብሩና ለሳይንስና ቴክኖሎጂ የተለየ ትኩረት እንዲሰጡ በሚያግዙ ፕሮጀክቶች ላይ በንቃት እንደሚሳተፉ አመልክቷል፡፡
የናጠጡት ባለጸጋ ዶናልድ ትራምፕ፣ በምርጫ ቅስቀሳቸው ወቅት፣ ካሸነፉ ደመወዛቸውን ጨርሶ እንደማይወስዱ ቃል መግባታቸውን  ያስታወሰው ዘገባው፤ ይሄም ሆኖ ግን የአገሪቱ ህግ፣ ፕሬዚዳንቶች ደመወዛቸውን እንዲወስዱ የሚያስገድድ በመሆኑ፣ ቃላቸውን ሙሉ በሙሉ ማክበር አልቻሉም ብሏል፡፡ ይኼን ተከትሎም፣ ሙሉ ደመወዛቸውን እየተቀበሉ  ለበጎ ምግባር ለመለገስ መወሰናቸውን ዘገባው ጠቁሟል፡፡

         43 የመንግስት ተቃዋሚ ግብጻውያን በእድሜ ልክ እስራት ተቀጡ

       የግብጹ ፕሬዚዳንት አብዱል ፈታህ አል ሲሲ፣ በአገሪቱ የድንበር ከተሞች የሚገኙ ተቋማትንና ፕሮጀክቶችን ከጥቃት ለመከላከል ታስቦ የተገነባውንና በመካከለኛው ምስራቅ አካባቢ በግዙፍነቱ ቀዳሚው እንደሆነ የተነገረለትን አዲስ የጦር ሰፈር መርቀው መክፈታቸውን አሶሼትድ ፕሬስ ዘግቧል፡፡
የተለያዩ የአረብ አገራት ከፍተኛ ባለስልጣናት በተገኙበት ባለፈው ሳምንት መጨረሻ ተመርቆ የተከፈተው ይህ የጦር ሰፈር፣ ከአሌክሳንድሪያ በስተምዕራብ በማርሳ ማትሮ ግዛት ውስጥ የሚገኝ ሲሆን፣ በአገሪቱ የመጀመሪያው ፕሬዚዳንት ሞሃመድ ኖጊብ ስም መሰየሙም ተነግሯል፡፡
የግብጽ መንግስት ታጣቂዎች ወደ ግዛቱ ሰርገው እንዳይገቡ ለመከላከል ሲል አገሪቱን ከሊቢያ ጋር በሚያዋስነው የድንበር አካባቢ ባራኒ የተባለ የጦር ሰፈር ማቋቋሙን በቅርቡ ማስታወቁንም ዘገባው አስታውሷል፡፡
በተያያዘ ዜና ደግሞ፣ በአገሪቱ የሚገኝ አንድ ፍርድ ቤት መንግስትን ተቃውመዋል ባላቸው 43 ዜጎች ላይ ባለፈው ማክሰኞ የዕድሜ ልክ እስራት ቅጣት ማስተላለፉን ሮይተርስ ዘግቧል፡፡ በ2011 መጨረሻ መንግስትን ተቃውመው በመዲናይቱ ካይሮ አደባባይ በመውጣት ብጥብጥ ፈጥረዋል፣ አመጽ ቀስቅሰዋል፣ በጸጥታ ሃይሎች ላይ ጥቃት አድርሰዋል በሚል የተከሰሱት ግለሰቦቹ፣ በወቅቱ በተፈጸመው ግጭት 17 ሰዎች ለህልፈተ ህይወት እንዲዳረጉና 2 ሺህ ያህል ሌሎች ግብጻውያን እንዲቆስሉ ሰበብ ሆነዋል መባሉን ዘገባው ገልጧል፡፡
ፍርድ ቤቱ ተከሳሾቹን በዕድሜ ልክ እስራት ከመቅጣቱ ባለፈም፣ በወቅቱ በህዝብ ተቋማት ላይ ለፈጸሙት የዝርፊያ ወንጀል በድምሩ ከ948 ሺህ ዶላር በላይ እንዲከፍሉ የገንዘብ ቅጣት እንደጣለባቸውም ዘገባው አመልክቷል፡፡ ሌሎች ከጉዳዩ ጋር በተያያዘ የተከሰሱ 9 ግብጻውያን በአስር አመት እስራት፣ አንድ ግለሰብ ደግሞ በአምስት አመት እስራት መቀጣቱንም ዘገባው አክሎ ገልጧል።

  ኳታር ባለፈው ወር በኤርትራና ጅቡቲ ድንበር ላይ አስፍራቸው የነበሩ ሰላም አስከባሪ ወታደሮቿን ማስወጣቷን ያስታወሰው አሶሼትድ ፕሬስ፣ ቻይና ይህንን ክፍተት ለመሙላት በአካባቢው የሰላም አስከባሪ ወታደሮችን ልታሰፍር እንደምትችል የአገሪቱ ከፍተኛ ዲፕሎማት ማስታወቃቸውን ዘግቧል፡፡
በአፍሪካ ህብረት የቻይና ከፍተኛ ዲፕሎማት ኩዋንግ ዌሊንን ጠቅሶ ዘገባው እንዳለው፣ ቻይና ጥያቄው ከቀረበላት በሁለቱ አገራት መካከል ለአመታት የዘለቀውን የድንበር ይገባኛል ውዝግብ ለመፍታት የአደራዳሪነት ሚናን ለመጫወትም ዝግጁ ናት፡፡
ቻይና ከግዛቷ ውጭ ያቋቋመቺው የመጀመሪያው የጦር ሰፈር ወደሆነውና ጅቡቲ ውስጥ ወደሚገኘው የጦር ሰፈር በዚህ ወር መጀመሪያ በርከት ያሉ ወታደሮቿን መላኳን ያስታወሰው ዘገባው፣ ይህም አገሪቱ የኢኮኖሚ ፍላጎት በምታሳይባቸው አካባቢዎች በምታደርገው የጦር ሃይል መስፋፋት ውስጥ እንደ አንድ ቁልፍ እርምጃ ተደርጎ እንደሚወሰድም ዘገባው አስታውሷል፡፡
ቻይና ምንም እንኳን በሰላም ማስከበር መስክ የአጭር ጊዜ ልምድ ቢኖራትም ከፍተኛ ቁጥር ያላቸው የሰላም አስከባሪ  ወታደሮችን ከሚያሰማሩ አምስት የተባበሩት መንግስታት ድርጅት የጸጥታው ምክር ቤት ቋሚ አባላት መካከል አንዷ መሆኗን ያስታወሰው ዘገባው፣ እስካለፈው ሰኔ ወር ድረስ በተመድ የሰላም ማስከበር ተልዕኮዎች ያሰማራቻቸው ወታደሮች ቁጥር ከ2 ሺህ 500 በላይ መድረሱንም አመልክቷል፡፡

 አሜሪካ በኢራንና በሩስያ ላይ አዳዲስ ማዕቀቦችን ለመጣል እየተዘጋጀች ባለችበት ወቅት፣ የሁለቱ አገራት መሪዎችና ከፍተኛ ባለስልጣናት ማዕቀብ የምትጥይብን ከሆነ ምላሻችን የከፋ ነው ሲሉ አሜሪካን አስጠንቅቀዋል፡፡
አሶሼትድ ፕሬስ ከቴህራን እንደዘገበው፣ የአሜሪካ ኮንግረስ በኢራን የባለስቲክ ሚሳኤል ፕሮግራም ላይ በተሳተፉ ግለሰቦች ላይ ለመጣል የታሰበውን ህግ የሚያጸድቀው ከሆነ፣ አገራቸው የከፋ ምላሽ እንደምትሰጥ የኢራኑ ፕሬዚዳንት ሀሰን ሩሃኒ ባለፈው ረቡዕ አስጠንቅቀዋል፡፡
ኢራን በባለስቲክ ሚሳኤል ፕሮግራሟ ላይ በሚሳተፉ ግለሰቦችና ከእነሱ ጋር የንግድ ግንኙነት ባለው ማንኛውም አካል ላይ የከፋ ቅጣትና ማዕቀብ ለመጣል በእንቅስቃሴ ላይ የምትገኘው አሜሪካ ያሰበቺውን የምታደርግ ከሆነ፣ አገራቸው ጥቅሟን ለማስከበር ስትል አፋጣኝ ምላሽ እንደምትሰጥ አስታውቀዋል፡፡ አሜሪካ በኢራን ላይ ለመጣል ባሰበቺው አዲሱ ማዕቀብ፣ በአገሪቱ የጦር ሃይል ላይ የሽብርተኝነት ማዕቀቦችን እስከመጣል እና የጦር መሳሪያ እገዳ እስከማድረግ የሚደርስ እርምጃ ልትወስድ እንደምትችል መነገሩንም ዘገባው አመልክቷል፡፡
ሩስያ በበኩሏ፣ አሜሪካ ልትጥልባት ያሰበቺው አዲስ ማዕቀብ በሁለቱ አገራት መካከል ያለውን የሻከረ ግንኙነት ወደ ከፋ ደረጃ ሊያሸጋግረው እንደሚችል ባለፈው ረቡዕ ማስጠንቀቋን ሮይተርስ ዘግቧል። የሩስያ ምክትል የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ሰርጊ ራብኮቭ፣ አሜሪካ በሩስያ ላይ ተጨማሪ ማዕቀቦችን ለመጣል እያደረገቺው የምትገኘው እንቅስቃሴ፣ በሁለቱ አገራት መካከል ያለውን ግንኙነት ለማሻሻል የሚቻልበትን ዕድል የሚያጨልምና ግንኙነቱን ወደባሰ መሻከር የሚያመራ እንደሆነ ባለፈው ረቡዕ ከኢንተርፋክስ የዜና ወኪል ጋር ባደረጉት ቃለ ምልልስ መናገራቸውን ዘገባው አስታውቋል፡፡
የአሜሪካ የማዕቀብ ዕቅድ ተግባራዊ የሚደረግ ከሆነ የሩስያ መንግስት ጉዳዩን በጥልቀት በመመርመር፣ በፕሬዚዳንት ፑቲን በሚሰጥ ውሳኔ ምላሽ የሚሰጥ መሆኑንም የፕሬዚዳንቱ ቃል አቀባይ ዲሚትሪ ፔስኮቭ ለጋዜጠኞች በሰጡት መግለጫ ማስታወቃቸው ተነግሯል፡፡
ፕሬዚዳንት ትራምፕ ወደ ስልጣን መምጣታቸውን ተከትሎ፣ በሁለቱ አገራት መካከል የነበረውን የሻከረ ግንኙነት ያሻሽሉታል የሚል ተስፋ የነበረ ቢሆንም፣ ሩስያ ባለፈው የአሜሪካ ፕሬዚዳንታዊ ምርጫ ጣልቃ ገብታለች በሚል የተፈጠረው አተካሮ ተስፋውን እንዳጨለመው ዘገባው አመልክቷል፡፡

 ‹‹ታላቁ ተቃርኖ›› የተሰኘ ፖለቲካዊ መፅሀፍ ገበያ ላይ ዋለ፡፡ ደራሲው ከቅርብ አመታት ወዲህ ታሪካዊ ልቦለድ ተብሎ በሚጠራው የስነ-ፅሁፍ ዘርፍ ተቀባይነት ያገኙትን ‹‹አውሮራ››፣ ‹‹የቀሳር እንባ›› እና ‹‹የሱፍ አበባ›› የተሰኙ በኢትዮ ኤርትራ፣ ጉዳይ፣ በኮሎኔል መንግስቱ ሀይለማሪያምና በኢህአፓ ዋና ዋና መስራቾች ዙሪያ የሚያጠነጥኑ ታሪኮች ያስነበቡ ሲሆን የአሁኑ ስራቸው ከታሪክ ልቦለድ ዘውግ ወጣ ብሎ አገሪቱ የገባችበትን ወቅታዊ የፖለቲካ ምስቅልቅል፣ ከስር መሰረቱ የሚተነትን ነው ተብሏል፡፡ በ400 ገፆች የተቀነበበው መፅሀፉ፤ በ119 ብር ለገበያ ቀርቧል፡፡

   የእውቋ ገጣሚ ረድኤት ተረፈ ወጋየሁ ‹‹አንድ ሐሙስ›› የተሰኘ የግጥም ስብስብ መፅሀፍ ሰሞኑን ለንባብ በቃ፡፡ በአገር ፍቅር ዙሪያ የሚያጠነጥኑ 52 ግጥሞችን የያዘው መድበሉ በ108 ገፆች ተመጥኖ በ47 ብርና በ20 ዶላር ለገበያ ቀርቧል፡፡
ገጣሚዋ ከዚህ ቀደም ከሌሎች ገጣሚዎች ጋር ‹‹መስቀል አደባባይ›› የተሰኘ የግጥም መፅሀፍ በጋራ ያሳተመች ሲሆን በአሁኑ ወቅት በሸገር ኤፍኤም የሚተላለፈው ‹‹አደረች አራዳ›› የሬዲዮ ሾው አዘጋጅ ናት፡፡ ገጣሚዋ በቅርቡ በብሔራዊ ቴአትር እየታየ በሚገኘው “ሲራኖ” የተሰኘ ትያትር ላይ እየተወነችም ትገኛለች፡፡