Administrator

Administrator

Monday, 20 October 2014 08:21

ዋሽንግተን - በአዲስ አበባ

        ለትምህርት ወደ አሜሪካ የሄዱት በወጣትነታቸው ነው - በ20 እና በ21 ዓመታቸው፡፡ ከአገር የወጡበትን ዓላማ ለማሳካት ኮሌጅ ገብተው ሴቷ ስለ አበባ፣ አትክልትና ፍራፍሬ (ሆርቲካልቸር)፣ ወንዱ ደግሞ ስለ ቴክኒክ ሙያ ተምረዋል፡፡
በአሜሪካ መኖር የሚቻለው እየሰሩ ነው፡፡ ያለበለዚያ ዶላር የሚመነዝር ቅልጥጥ ያለ የከበርቴ ልጅ መሆን የግድ ነው፡፡ ወጣቶቹ እንደዚያ ስላልሆኑ፣ ተግተው መሥራት ነበረባቸው፡፡ በዋሺንግተን ዲሲና ሜሪላንድም “አዲስ አበባ” የተባለ ምግብ ቤት ከፍተው የኢትዮጵያን ባህልና ምግብ በማስተዋወቅ ከ30 ዓመት በላይ እየሰሩ ኖረዋል፡፡
ዕድሜአቸውን በሙሉ በውጭ አገር መኖር አልፈለጉም፡፡ ወደ አገራቸው ተመልሰው በቋጠሯት ገንዘብ ኢንቨስት በማድረግ፣ ለወገኖቻቸው የሥራ ዕድል በመፍጠር፣ ለአገራቸው ዕድገት የበኩላቸውን አስተዋፅኦ ለማበርከት ወሰኑ፡፡
ወ/ሮ ወርቅነሽ ጌታቸውና አቶ አስፋው አምዴ የተወለዱት በአዲስ አበባ ከተማ ነው፡፡ አቶ አስፋው፣ በቀድሞው ልዑል መኮንን በአሁኑ አዲስ ከተማ መሰናዶ ት/ቤት የ2ኛ ደረጃ ትምህርታቸውን አጠናቀው ወደ አሜሪካ የሄዱት እ.ኤ.አ በ1970 ዓ.ም ነው፡፡
ወ/ሮ ወርቅነሽ ደግሞ 1ኛ ደረጃን በአርበኞች ት/ቤት፣ 2ኛ ደረጃን በቀድሞው እቴጌ መነን፣ በአሁኑ የካቲት 12 መሰናዶ ት/ቤት ጨርሰው ወደ አሜሪካ ዋሽንግተን የተጓዙት ከአምስት ዓመት በኋላ ነበር፡፡
በዚያው ዓመት ነበር ሁለቱ ጥንዶች የተዋወቁት፡፡ ከዚያም እንደ ድርጅትም እንደ ማህበረሰብም ሆነው ከዚህ የሚሄዱትን ኢትዮጵያውያን በመቀበል፣ አገሪቷንም ለአሜሪካ በማስተዋወቅ በአምባሳደርነት ሲያገለግል የቆየውንና ታዋቂውን “አዲስ አበባ ምግብ ቤት” እ.ኤ.አ በ1984 ዓ.ም በዋሽንግተን ዲሲ መክፈታቸውን ይናገራሉ፡፡
እዚያም የኢትዮጵያን ምግብና ባህል በማስተዋወቅ ለ21 ዓመት ሰሩ፡፡ ምግብ ቤቱ የበለጠ ታዋቂ እየሆነ፣ የሚያስተናግደው አበሻም ሆነ ፈረንጅ እየጨመረ ሲሄድ፣ መኪና ማቆሚያ ቦታ ጠበበ፡፡
 በ2005 ዓ.ም ሜሪላንድ ወደተባለችው ከተማ ተዛውረው፣ እዚያም ታዋቂውን አዲስ አበባ ምግብ ቤት መክፈታቸውን ተናግረዋል፡፡ በሜሪላንድ 8 ዓመት ከሰሩ በኋላ ነው ጓዛቸውን ጠቅልለው ወደ አዲስ አበባ የመጡት፡፡ጥንዶቹ ከ10 ዓመት በፊት ቦታ ገዝተው የሆቴል ግንባታ ጀመሩ፡፡
70 የመኝታ ክፍሎች ያሉትና አትላስ አካባቢ የሚገኘው ዋሺንግተን ሆቴል ሥራ የጀመረው በቅርቡ ቢሆንም በሚሰጠው ደረጃውን የጠበቀ አገልግሎት በህብረተሰቡ ዘንድ ጥሩ ተቀባይነት እያገኘ መሆኑን ወ/ሮ ወርቅነሽ ይናገራሉ፡፡
ለስብሰባ፣ ለመዝናናትም ሆነ ለሥራ… ከውጭ ለሚመጡ መሪዎች፣ ዲፕሎማቶችና የቢዝነስ ሰዎች ያዘጋጀነው 5ኛና 6ኛ ፎቅ ያሉት ቪአይፒ ክፍሎች እኛን ከሌሎች ሆቴሎች ይለዩናል ያሉት ወ/ሮ ወርቅነሽ፤ በሁለቱ ፎቆች ያሉት ክፍሎች ለአንድ መሪ ቤተሰብ፣ ባለሥልጣናትና አጃቢዎች ወይም ለአንድ አገር ዲፕሎማትና አብረውት ለሚመጡ የሥራ ኃላፊዎች ወይም ለአንድ አገር የቢዝነስ አባላት ቡድን … የሚከራዩ እንደሆነ ገልፀዋል፡፡ቪአይፒ ክፍሉ የራሱ ሳሎን፣ የራሱ ምግብ ማብሰያ (ኪችን) ለቤተሰብና አብረው ላሉ እንግዶች የሚሆኑ 5 መኝታ ክፍሎች፣ ጃኩዚ፣ ስቲምና ሳውና ባዝ፣ ዋና መኝታ ቤት፣ የራሱ ባርና መዝናኛ ቴራስ፣ ልዩ የደህንነት ጥበቃ… ያሉት መሆኑን ገልፀዋል፡፡
አሁን ያልተጠናቀቁ ነገሮች ስላሉ ሁሉም ነገር ሲያልቅ ሆቴሉ በጠቅላላ 180 ሚሊዮን ብር ይፈጃል ያሉት አቶ አስፋው፤ ዋሺንግተን በነበረው አዲስ አበባ የባህል ምግብ ቤት የተሰየመው የምግብ አዳራሽ ሁሉንም ዓይነት ባህላዊ ምግቦች ያዘጋጃል ብለዋል፡፡
 ኮሎምቢያ በማለት የበሰየሙት ዘመናዊ ሬስቶራንት ከ40 በላይ የውጭ አገር ምግቦች እንደሚያዘጋጅ፣ ሁለት ባር እንዲሁም በመቅደላ የተሰየመ ትልቅ አዳራሽ፣ ጆርጅታውን ጂምና ስፓ፣ አዲስ አበባን 360 ዲግሪ እያዩ የሚዝናኑበትና በ18 ዲስትሪክት የተሰየመ ቴራስ ሬስቶራንትና ባር፣ … እንዳሉት ገልጸው፤ ሆቴሉንና የተለያዩ አገልግሎት መስጪያዎችን በውጭ አገር ስሞች የሰየሟቸው ለብዙ ዓመታት የሚያውቋቸውን የአሜሪካ አካባቢዎች ለማስታወስ እንደሆነ አስረድተዋል፡፡የሆቴሉ ምግብ በእንግዶች የተወደደ ንፁህ፣ ጣፋጭና ጥራቱን የጠበቀ ቢሆንም ዋጋው ተመጣጣኝ በመሆኑ ኪስ አይጐዳም፣ አንድ ምግብ በ150 ብር መመገብ ይቻላል፣ ከዚያም በታች አለ ብለዋል፡፡
የመኝታ ክፍሎቹ ዋጋ ሲንግል ቤድ 95 ዶላር፣ ደብል ቤድ 120 ዶላር፣ ሱት ክፍሎች 160 ዶላር፣ ልዩ የሆነው ቪአይፒ 950 ዶላር እንደሆኑ ጠቅሰው፣ ስብሰባ ሲኖርና አስጐብኚ ድርጅቶች በርከት ያሉ እንግዶች ሲያመጡ የዋጋ ቅናሽ እንደሚደረግ ተናግረዋል፡፡
ሆቴሉን ሲሰሩ ነገሩ ሁሉ አልጋ በአልጋ እንዳልነበረ የጠቀሱት አቶ አስፋው፤ መንግሥት ኢንቨስትመንትን ለማበረታታት በሰጠው ዕድል ቋሚ ዕቃዎችን ከቀረጥ ነፃ እንዳስገቡ ገልፀው፣ ከባንክ ብድር ማግኘት፣ የጉምሩክ ቢሮክራሲ፣ ባለሙያ የሆነ የኮንስትራክሽን ሠራተኛ እጥረት… ዋና ዋናዎቹ ችግሮች እንደነበሩ ገልፀዋል፡፡ ሆቴሉ ለ130 ዜጎች የሥራ ዕድል እንደፈጠረም ለማወቅ ተችሏል፡፡      

      በአሜሪካ በመጪው ወር ለሚካሄደው የግዛትና የኮንግረስ ምርጫ የሚወዳደሩ ጥቁር ፖለቲከኞች ቁጥር ክብረ ወሰን ማስመዝገቡንና የፖለቲካ ተንታኞችም፣ ባራክ ኦባማ በምርጫ አሸንፈው በአገሪቱ ታሪክ የመጀመሪያው ጥቁር ፕሬዚዳንት መሆናቸው በጥቁር አማሪካውያኑ ላይ ለታየው የፖለቲካ ተሳትፎ እድገት አስተዋጽኦ አበርክቷል ማለታቸውን አሶሼትድ ፕሬስ ዘገበ፡፡
በሁለቱ ምርጫዎች የሚሳተፉ ጥቁር ዕጩ ተወዳዳሪዎች ከ100 በላይ መሆኑን የጠቆመው ዘገባው፣ 83 ያህል ጥቁር የሪፐብሊካንና የዲሞክራቲክ ፓርቲ ተወካዮች ለአሜሪካ ምክር ቤት እንደሚወዳደሩና ይህም በታሪክ ታይቶ የማይታወቅ እንደሆነ አስታውቋል፡፡25 ያህል አፍሪካ አሜሪካውያን በተለያዩ የአገሪቱ ግዛቶች ለሴናተርነት፣ ለገዢነት ወይም ለሌተናንት ገዢነት ስፍራዎች እንደሚወዳደሩና፣ ይህም በአገሪቱ የምርጫ ታሪክ ከፍተኛ እንደሆነ ዘገባው ገልጧል፡፡ከዚህ ቀደም ለአሜሪካ ምክር ቤት አባልነት በርካታ ጥቁሮች የተወዳደሩበት እንደሆነ የተመዘገበው፣ እ.ኤ.አ በ2012 የተካሄደውና ፕሬዚዳንት ኦባማ ለሁለተኛ ዙር አሸንፈው በስልጣን መቀጠላቸውን ያረጋገጡበት ምርጫ ሲሆን  በዚህ ምርጫ ተወዳዳሪ ሆነው የቀረቡት ጥቁሮች 72 እንደነበሩ ዘገባው አስታውሷል፡፡ በግዛቶች ምርጫ በርካታ ጥቁሮች የተወዳደሩበት አመት እ.ኤ.አ 2002 እንደነበረ ጠቁሞ፣ በወቅቱ የተወዳዳሪዎች ቁጥር 17 እንደነበርም አስረድቷል፡፡ የኮሎምቢያ ዩኒቨርሲቲ የአፍሪካን አሜሪካን ፖለቲክስ ኤንድ ሶሳይቲ ማዕከል ዳይሬክተር  ፕሮፌሰር ፍሬዴሪክ ሲ ሃሪስ፣ ፕሬዚዳንት ባራክ ኦባማ ወደ ስልጣን መምጣታቸው ጥቁሮች በምርጫ ድምጽ እንዲሰጡና  ጥቁር ፖለቲከኞችም ከዚህ ቀደም በጥቁሮች ተይዘው በማያውቁ የአገሪቱ ከፍተኛ የስልጣን ቦታዎች ላይ ለመቀመጥ እንዲወዳደሩ እንዳነሳሳቸው ተናግረዋል፡፡

     ባለፈው ሳምንት የኖቤል የሰላም ሽልማት የተቀበለችው ፓኪስታናዊቷ የህጻናት መብቶች ተሟጋች ማላላ ዮሱፋዚ፣ የናይጀሪያ መንግስትና አለማቀፉ ማህበረሰብ ቦኮ ሃራም በተባለው አሸባሪ ቡድን የታፈኑትን 219 የአገሪቱ ልጃገረዶች በአፋጣኝ ለማስለቀቅ በስፋት እንዲንቀሳቀሱ ጥሪ ማቅረቧን ቢቢሲ ዘገበ፡፡የመብት ተሟጋቾች ከስድስት ወራት በፊት በታጣቂዎች ታፍነው የተወሰዱትና አሁንም ድረስ በአሸባሪዎች ቁጥጥር ስር የሚገኙት የአገሪቱ ልጃገረዶች ነጻ እንዲወጡ ከመቸውም ጊዜ በበለጠ ድምጻቸውን እንዲያሰሙ ጥሪ ያቀረበችው ማላላ፣ ልጃገረዶቹ ከቤተሰቦቻቸው ጋር መቀላቀልና ጥራትና ደህንነቱ የተጠበቀ ትምህርት ማግኘት ይገባቸዋል ብላለች፡፡“የአገሪቱ መንግስት እና አለማቀፉ ማህበረሰብ ለችግሩ አፋጣኝና ሰላማዊ መፍትሄ ለማስገኘት የሚያደርጉትን ጥረት በከፍተኛ ሁኔታ እንዲያሳድጉ እጠይቃለሁ” ብላለች ማላላ፡፡ማላላ ባለፈው ሃምሌ ወር ወደ ናይጀሪያ በማምራት በጉዳዩ ዙሪያ ከአገሪቱ ፕሬዚዳንት ጉድላክ ጆናታን ጋር መወያየቷን የጠቆመው ዘገባው፣ ልጃገረዶቹ ባለፈው ሚያዝያ በሰሜን ምስራቃዊ ናይጀሪያዋ ቺቦክ ከተማ ወደሚገኘው የአዳሪ ትምህርት ቤታቸው በመጓዝ ላይ ሳሉ  በቦኮ ሃራም ታጣቂዎች መጠለፋቸውን አስታውሷል፡፡
የናይጀሪያ መንግስት ልጃገረዶቹን ለማስለቀቅ በቂ ጥረት አላደረገም የሚል ትችት እንደሚሰነዘርበት የጠቀሰው ቢቢሲ፤ጉዳዩ የሚመለከታቸው የአገሪቱ ሚኒስትሮች ግን ትችቱን እንዳጣጣሉት አመልክቷል፡፡በቅርቡ “ልጃገረዶቻችንን መልሱልን” የሚል ዘመቻ ያዘጋጁ የናይጀሪያ የመብት ተሟጋቾች፣ መንግስት አፋጣኝ እርምጃ እንዲወስድ ለመጠየቅ አቡጃ  ወደሚገኘው የአገሪቱ ፕሬዚዳንት ቤት ማምራታቸውን ያስታወሰው ዘገባው፣ ፖሊሶች ወደ ስፍራው እንዳይደርሱ እንደከለከሏቸው አክሎ ገልጧል፡፡

      በምዕራብ አፍሪካ አገራት የተቀሰቀሰው የኢቦላ ቫይረስ ተጠቂዎች ቁጥር እስከ ነገ ከ9ሺህ በላይ ይደርሳል  ተብሎ እንደሚጠበቅ የአለም የጤና ድርጅትን ጠቅሶ ሮይተርስ ዘገበ፡፡
ባለፈው መጋቢት ወር በጊኒ የተከሰተውና በምዕራብ አፍሪካ በመስፋፋት ላይ የሚገኘው የኢቦላ ወረርሽኝ እስካሁን ድረስ 8ሺህ 914 ሰዎችን እንዳጠቃና ከነዚህ ውስጥም 4ሺህ 447 ያህሉ ለህልፈት እንደተዳረጉ የጠቆመው ዘገባው፣  ቁጥሩ ዛሬና ነገ ከ9ሺህ በላይ ይደርሳል ተብሎ እንደሚጠበቅ ገልጧል፡፡
የአለም የጤና ድርጅት ረዳት ዳይሬክተር ብሩስ አይልዋርድ እንዳሉት፣ ቫይረሱ በከፍተኛ ሁኔታ በተከሰተባቸው አንዳንድ አካባቢዎች አዳዲስ ሰዎችን የማጥቃቱ ሁኔታ እየቀነሰ መሆኑን የሚያሳዩ ምልክቶች ቢኖሩም፣ ወደ ሌሎች ቦታዎች እየተስፋፋ በመሆኑ በበሽታው የሚጠቁ ሰዎች ቁጥር እየጨመረ ይሄዳል ተብሎ ይጠበቃል፡፡
ድርጅቱ እንደተነበየው፤ የኢቦላ ቫይረስ ስርጭት በዚሁ ከቀጠለ በየሳምንቱ በቫይረሱ የሚያዙ ሰዎች ቁጥር በአጭር ጊዜ ውስጥ እስከ አስር ሺህ ሊደርስ ይችላል፡፡
የአለም የጤና ድርጅት ኢቦላ በተስፋፋባቸው የምዕራብ አፍሪካ አገራት በቫይረሱ የተጠቁና የሞቱ ሰዎችን በተመለከተ ይፋ እየተደረጉ ያሉ መረጃዎች፣ የተዛቡና ከትክክለኛው ቁጥር ያነሱ ናቸው ማለቱን የጠቆመው ዘገባው፤ ይህም ችግሩን ለመቅረፍ ተገቢው ጥረት እንዳይደረግ የሚያዘናጋ ነው ብሏል፡፡
ፕሬዚዳንት ባራክ ኦባማ በበኩላቸው ባለፈው ረቡዕ በኢቦላ ዙሪያ ለመምከር በዋይት ሃውስ በጠሩት አስቸኳይ ስብሰባ፣ ከአገሪቱ ከፍተኛ ባለስልጣናትና የጤና ባለሙያዎች ጋር የተወያዩ ሲሆን፣ የቫይረሱን ስርጭት መግታት ጊዜ የማይሰጠው መሆኑንና የአገሪቱ መንግስትም ኢቦላ በከፍተኛ ሁኔታ እንደሚያሳስበው መግለጻቸውንም ቢቢሲ ዘግቧል፡፡ የቫይረሱን ስርጭት ለመግታት ከሲዲሲና ከሚመለከታቸው የአገሪቱ የመንግስት መስሪያ ቤቶችና ተቋማት የተውጣጡ ባለሙያዎችን ያካተተ ብሄራዊ ግብረሃይል አቋቁመው በአፋጣኝ ወደ ስራ መግባታቸውንም ገልጸዋል፡፡ፕሬዚዳንቱ ባለፈው ማክሰኞ በሰጡት መግለጫ፣ አለማቀፉ ማህበረሰብ ኢቦላን ለመዋጋት ተገቢውን ድጋፍ እያደረገ እንዳልሆነ ገልጸው፣ ተገቢውን ድጋፍ እንዲያደርጉ የተለያዩ የዓለም አገራት መሪዎችን እንደሚያግባቡ መናገራቸውን ቢቢሲ አስታውሷል፡፡ቢቢሲ ከአፍሪካ ውጭ ያለውን የኢቦላ ክስተት በተመለከተ ከትናንት በስቲያ ባወጣው መረጃ እንዳለው፣ የዘንድሮው ወረርሽኝ ከተቀሰቀሰበት ጊዜ አንስቶ እስካሁን ድረስ በአሜሪካ 8፣ በጀርመን 3፣ በስፔን 3፣ በኖርዌይ 1፣ በፈረንሳይ 1 እና በእንግሊዝ 1 በድምሩ 17 ሰዎች በኢቦላ የተያዙ ሲሆን፤ ከእነዚህ ውስጥም አንድ አሜሪካዊ፣ አንድ ጀርመናዊና ሁለት ስፔናውያን ለህልፈት ተዳርገዋል፡፡ ከሶስቱ ሰዎች በስተቀር ሁሉም በቫይረሱ የተያዙት ወደ ምዕራብ አፍሪካ አገራት በሄዱበት ወቅት ነው ተብሏል፡፡
በሌላ በኩል ደግሞ የታዋቂው የማህበረሰብ ድረገጽ የፌስቡክ መስራች ማርክ ዙክበርግ የኢቦላን ወረርሽኝ ለመግታት የተጀመረውን ጥረት ለማገዝ የሚውል የ25 ሚሊዮን ዶላር የገንዘብ ድጋፍ ማድረጉን ብሉምበርግ ኒውስ ዘግቧል፡፡
ዙክበርግና ባለቤቱ ፕሪስኪላ ቻን ገንዘቡን ለአሜሪካው ሲዲሲ ፋውንዴሽን ያስረከቡ ሲሆን፣ የህክምና ማዕከላትን ለማቋቋምና አፍሪካውያን ባለሙያዎችን ለማሰልጠን የመሳሰሉ ስራዎች እንደሚውል ተነግሯል፡፡
“ኢቦላ የበለጠ ከመስፋፋቱና አለማቀፍ የጤና ቀውስ ከመሆኑ በፊት በአፋጣኝ በቁጥጥር ውስጥ ልናውለው ይገባል” ብሏል ዙክበርግ በፌስቡክ ገጹ ላይ ባስተላለፈው መልዕክት፡፡





    “ሬድ ቡል”ን የመሳሰሉ ሃይል ሰጪ መጠጦች በተለይ ከአልኮል መጠጥ ጋር ተደባልቀው ሲጠጡ የጤና ችግር ሊያስከትሉ እንደሚችል የዓለም ጤና ድርጅት ተመራማሪዎች አስጠነቀቁ፡፡
በአውሮፓ የተደረገ ጥናት እንዳረጋገጠው፣ ከ70 በመቶ በላይ የሚሆኑ እድሜያቸው ከ18-29 ዓመት የሚደርሱ ወጣቶች፣ እንደ “ሬድ ቡል” ያሉ ሃይል ሰጪ መጠጦችን (Energy drinks) ከአልኮል መጠጥ ጋር እየደባለቁ ይጠጣሉ፡፡
የዓለም ጤና ድርጅት ጥናት እንደሚለው፤ ዋነኛው የስጋት ምንጭ በመጠጦቹ ውስጥ ያለው ከፍተኛ የካፌይን መጠን ሲሆን ይሄም ፈጣን ወይም ያልተመጣጠነ የልብ ምት፣ ከፍተኛ የደም ግፊት፣ ማስመለስ፣ ከፍተኛ የሰውነት መንቀጥቀጥና ባስ ሲልም ለሞት የሚዳርግ የልብ በሽታ… የመሳሰሉ የጤና ችግሮችን ሊያስከትል ይችላል፡፡
ካፌይን በህፃናት ላይ በጥናት የተረጋገጠ አሉታዊ ተፅአኖ እንዳለው ተመራማሪዎቹ በጥናት ሪፖርታቸው ላይ ጠቁመዋል፡፡
“የሃይል ሰጪ መጠጦች ተወዳጅነት መጨመር ያደረሰው ሙሉ ተፅእኖ ገና በቁጥር አልተቀመጠም፤ ነገር ግን ወጣቶችን ዒላማ ያደረገው የሃይል ሰጪ መጠጦች ጠንካራ የገበያ ስልት በምርቶቹ ላይ ከሚደረግ ውስንና ተለዋዋጭ ቁጥጥር ጋር ሲዳመር እነዚህ መጠጦች ለህብረተሰቡ ጉልህ የጤና ስጋት የሚሆኑበትን ድባብ ፈጥሯል” ብለዋል - ተመራማሪዎቹ፡፡
ዩሮሞኒተር ባሰፈረው መረጃ መሰረት፣ የሃይል ሰጪ መጠጦች ዓለም አቀፋዊ ሽያጭ እ.ኤ.አ በ1991 ዓ.ም ከነበረው 2.4 ቢሊዮን ፓውንድ በ2013 ዓ.ም ወደ 17.3 ቢሊዮን ፓውንድ አሻቅቧል፡፡ “ሬድ ቡል” የተባለው ሃይል ሰጪ መጠጥ በእንግሊዝ በከፍተኛ ሽያጫቸው ከሚታወቁ ለስላሳ መጠጦች በሦስተኛ ደረጃ ላይ እንደሚገኝ ተጠቁሟል፡፡
አንዳንድ የቡና ዘሮች ተመሳሳይ የካፌይን መጠን ያላቸው ቢሆንም ሃይል ሰጪ መጠጦች ቀዝቃዛውን የሚጠጡ በመሆናቸው በከፍተኛ ፍጥነት የሚወሰዱ ናቸው ብሏል - ጥናቱ፡፡
የዓለም ጤና ድርጅት የጥናት ቅኝት እንደሚለው፤ እስካሁን የሚታወቁት ሃይል ሰጪ መጠጦች ካላቸው የካፌይን መጠን በእጅጉ የላቀ ካፌይን የያዙ አዳዲስ ምርቶች እየተበራከቱ መጥተዋል፡፡
ሃይል ሰጪ መጠጦች ከካፌይን በተጨማሪ ጉዋራና፣ ታውሪንና ቢ ቪታሚንስ የተባሉ ንጥረነገሮችን እንደያዙ የሚናገሩት ተመራማሪዎቹ፤ ስለምንነታቸውና ከካፌይን ጋር ስላላቸው መስተጋብር ለማወቅ ተጨማሪ ምርምር ያስፈልጋል ብለዋል፡፡
የዓለም የጤና ድርጅት ፖሊሲን አይወክልም በተባለ የጥናት ፅሁፍ ላይ እንደተጠቆመው፣ ሃይል ሰጪ መጠጦችን ከአልኮል መጠጥ ጋር ደባልቆ በመጠጣት ጉዳት እንደሚደርስ የሚያሳዩ ማስረጃዎች እየጨመሩ መጥተዋል፡፡ የአውሮፓ የምግብ ደህንነት ባለስልጣን ጥናት፤ ከ70 በመቶ በላይ የሚሆኑ እድሜያቸው ከ18-29 የሚደርሱ ወጣቶች ሃይል ሰጪ መጠጦችን ከአልኮል ጋር ደባልቀው እንደሚጠጡ አረጋግጧል፡፡
አጥኚዎቹ እንደሚሉት፤ አልኮል ብቻውን ከመጠጣት የበለጠ ይሄኛው በጣም አደገኛ ነው፤ ምክንያቱም የስካሩ መጠን ባይቀንስም ሰዎች መስከራቸውን ለማወቅ እንዲቸገሩ ያደርጋቸዋል፡፡
ሃይል ሰጪ መጠጦች በአብዛኛው የስፖርት ብቃትን እንደሚጨምሩ እየተነገረ ቢተዋወቁም ከአካል እንቅስቃሴ ጋር ሲጣመሩ ለአደጋ ሊያጋልጡ እንደሚችሉ ጥናቱ አክሎ ገልጿል፡፡
በእነዚህ መጠጦች ውስጥ መካተት ያለበት የካፌይን መጠን ምን ያህል እንደሆነ ተመራማሪዎቹ በቁጥር ባይገልፁም በጥናት ላይ የተመሰረተ መሆን እንዳለበት ጠቁመዋል፡፡
በእንግሊዝ የምግብ ጥራት መመዘኛ አጀንሲ፣ ከታህሳስ ወር ጀምሮ ከፍተኛ የካፌይን መጠን የያዙ ሃይል ሰጪ መጠጦች፣ ይሄንኑ በምርቶቻቸው ላይ እንዲጠቁሙና “ለህፃናት ወይም ለነፍሰጡር ወይም ጡት ለሚያጠቡ ሴቶች አይመከርም” የሚል ማስጠንቀቂያ እንዲያሰፍሩ ያስገድዳል ተብሏል፡፡ በግንቦር ወር ደግሞ ሉቱዋኒያ እንዲህ ያሉ መጠጦች እድሜያቸው ከ18 ዓመት በታች ለሆኑ ህፃናት እንዳይሸጥ የሚያግድ ህግ በማውጣት የመጀመሪያዋ የአውሮፓ አገር ትሆናለች ተብሎ ይጠበቃል፡፡

Monday, 20 October 2014 08:04

የፍቅር ጥግ

(ስለውበት)

ውበት  እውነት ነው፤ እውነትም ውበት፡፡
ጆን ኪትስ
ውበትን የምትመለከት ነፍስ አንዳንዴ ብቻዋን ልትጓዝ ትችላለች፡፡
ገተ
ፍቅር በውስጥህ ስለሚበቅል ውበትም እዚያው ይበቅላል፡፡ ፍቅር የነፍስ ውበት ነውና፡፡
ቅዱስ ኦገስቲን
የሴቶች ትህትና በአጠቃላይ ከውበታቸው ጋር ይጨምራል፡፡
ፍሬድሪክ ኒቼ
ውበት ያለው ፊት ላይ አይደለም፤ ውበት ልብ ውስጥ ያለ ብርሃን ነው፡፡
ካህሊል ጀብራን
ውብ የሆነ ማንኛውም ነገር የማየት ዕድል አያምልጥህ፤ ውበት የእግዚአብሔር የእጅ ፅሁፍ ነውና፡፡
ራልፍ ዋልዶ ኤመርሰን
ፈገግታዋ የማይከደንና ገፅታዋ ደስታ የማይርቀው ሴት፣ ምንም ብትለብስ ማማሯ አይቀርም፡፡
አኔ ሮይፊ
በዓለም ላይ ያሉ ምርጥና እጅግ ውብ የሆኑ ነገሮች በዓይን መታየትና በእጅ መዳሰስ አይችሉም፤ በልብ ነው መጣጣም ያለባቸው፡፡
ሔለን ከለር
ውበት ዓይንን ብቻ ሲያስደስት፤ ሸጋ ስብዕና ነፍስን ይማርካል፡፡
ቮልቴር
በእርግጠኝነት ለውበት ፍፁም የሆነ መለኪያ የለውም፡፡ ይሄም ነው ፍለጋውን እጅግ አጓጊ የሚያደርገው፡፡
ጆን ኬኔዝ ጋልብሬይዝ
የውበትን ያህል በቀጥታ ወደ ነፍስ የሚጓዝ ምንም ነገር የለም፡፡
ጆሴፍ አዲሶን

       ከእለታት አንድ ቀን አንድ የፐርሺያ ንጉሥ ሁለት ሰዎች ላይ የሞት ፍርድ ፈረደባቸው ይባላል፡፡ በመጨረሻም፤
“የሞት ፍርዱ ከመፈፀሙ በፊት የፈለጋችሁትን ተናገሩ” ሲል እድል ይሰጣቸዋል፡፡
አንደኛው፤ “ምንም የምናገረው የለኝም” አለ
ሁለተኛው፤ ንጉሡ ምን ያህል ፈረሳቸውን እንደሚወዱት ስለሚያውቅ፤
“ንጉሥ ሆይ የአንድ ዓመት ጊዜ ከሰጡኝ ፈረስዎ ወደሰማይ እየከነፈ እነዲሄድ ላስተምረው እችላለሁ” አላቸው፡፡
ንጉሡ በሰማይ ላይ የሚከንፍ ፈረስ እየጋለቡ ሲሄዱ ታያቸው፡፡ ካሁኑ ነሸጣቸውና ይቁነጠነጡ ጀመር፡፡
“ይሁን አንድ ዓመት ሰጥተንሃል፡፡ ፈረሱን አምጥተው እንዲያስረክቡህ አደርጋለሁ” አሉ፡፡
የመጀመሪያው እሥረኛ በምንም አይነት ፈረስ እንደማይበር ስለሚያውቅ ፈረስ አስተማሪውን እሥረኛ ጓደኛውን እንዲህ ሲል ጠየቀው፤
“ወዳጄ፤ ፈረስ በሰማይ እንደማይበር አሳምረህ ታውቃለህ፡፡ እንዲህ ያለ የዕብድ ሀሳብ ከየት አምጥተህ ነው ቃል የገባኸው፡፡ የመሞቻችንን ጊዜ ከማራዘም በስተቀር ምን ይፈይድልሃል?”
ፈረስ አስተማሪውም፤
“አይምሰልህ ወዳጄ፤ ነፃነቴን የማገኝባቸውን አራት ዕድሎች ራሴ መስጠቴ ነው”
አንደኛው እሥረኛም፤
“አራቱ ዕድሎች ምን ምን ናቸው?” ሲል በመጓጓት ጠየቀው፡፡
ፈረስ አስተማሪው፤ እንዲህ ሲል ዘረዘረለት፡-
1ኛ ወይ በዚህ ዓመት ውስጥ ንጉሡ ሊሞቱ ይችላሉ
2ኛ እኔም ልሞት እችላለሁ
3ኛ ወይ ደሞ ፈረሱም ሊሞት ይችላል
4ኛ ደሞስ ማን ያውቃል እኔ ፈረሱ በሰማይ እንዲበር ላስተምረው እችል ይሆናል
***
አበው ጠበብት ሦስት አይነት ጊዜ አለ ይሉናል፡፡ አንደኛው ረዥም ጊዜ የሚባለው ነው፡፡ ረዥም ጊዜ በትዕግሥት በጥንቃቄ እቅዶቻችንን ሁሉ ቀምረን የምንጓዝበት ጊዜ ነው፡፡ ሁለተኛው ተገደን የምንገባበት ጊዜ ነው፡፡ (Forced Time የሚሉት ነው ፈረንጆች፡፡) ይሄ አጭርና ጉዳያችንን ተጣድፈን፣ ተወጥረን በግዴታ ወደ ተግባር የምናስገባበት ነው፡፡ ሦስተኛው የፍፃሜ ጊዜ ነው፡፡ እቅዶችን የምንፈፅምበትና ግባችንን የምንመታበት ነው፡፡ እነዚህን ጊዜያት ወደ አገር መንዝረን ስናያቸው “ከእቅድ በላይ አመረትን”፣ “ከታሰበው ገዜ ቀደም ብለን ግባችንን መትተናል”፣ “ሥር-ነቀል ለውጥ አካሂደን ሰፊውን ህዝብ የአብዮቱ ተጠቃሚ አድርገነዋል”… ወዘተ በማለት አያሌ መፈክሮችን ስናሰግር መክረማችንን እንድንመረምር ግድ ይለናል፡፡ በእርግጥ ግን ያቀድነውን እቅድና ጊዜያችንን በአግባቡ አጣጥመን ለአንዳች ፋይዳ በቅተናልን? ተጀምረው የተቋረጡ “እንደ እገሌ ህንፃ አቁሞ ያስቀርሽ!” “እንደ እገሌ መንገድ ያሽመድምድህ!” “እንደ አገሬ መብራት ድፍን ያርገኝ ብለህ ማል እስቲ!” “እንደ ዛሬው ውሃ ድርቅ ያርገኝ በል እስቲ!” “እንደ ኔትወርካችን ይበጣጥሰኝ! በል…” እስከመባባል ድረስ በምፀት፣ በስላቅና፣ በለበጣ ህይወት ውስጥ የምንጓዘው ከቶም እቅዳችን በጊዜው ተከናውኖ ነውን? ያሰኘናል፡፡
ናፖሊዮን ቦናፓርት “የተነጠቅነውን ቦታ ለማስመለስ እንችላለን፣ ያጠፋነውን ጊዜ ግን በጭራሽ” ይለናል፡፡ የበለጠ የከፋው ደግሞ ስለባከነው ሰዓት በመገማገም የምናባክነው ሰዓት ነው፡፡ ባለፈው መንግሥት “የኮሚቴዎችን መብዛትና እንዴት እንደሚቀነሱ የሚያጠና ኮሚቴ ፍጠሩ!!” እንደተባለው ነው፡፡
“ጊዜ የሥልጣን እጅ ነው፣ የሚያውቅ ሎሌው ያረገዋል
የተጃጃለውን ግና፣ ሎሌው አርጐ ይገዛዋል” ይለናል ገጣሚው፡፡ ይህን ልብ እንበል፡፡
የሙሰኞች መናኸሪያ የሆነችው አገራችን የጊዜ ሌቦችም መደበቂያ መሆኗንም አንዘንጋ፡፡ ሙስና ከየትም የሚከሰት ተዓምት ሳይሆን የሰው ልጆች ራሳቸው ጊዜን እያዩ የሚፈፅሙት እኩይ ተግባር ነው፡፡ ዞሮ ዞሮ የሚያጠፋም ሰው፣ የሚያለማም ሰው ነው፡፡ ሰው የምንለው ከልሂቅ እስከ ደቂቅ ነው”
“ለመቶ አምሳ ጌታ፣
ስታጠቅ ስፈታ
ነጠላዬ…
አለቀ በላዬ”
ካለችው የበታች አካል ጀምሮ፤
“የእባብ መርዝም እንደዚያው፤ ሁሌም የሚፈለፈለው
ንጉሡ አናት ላይ ካለው፤ ከዘውዱ ወይራ ቅጠል ነው”
እስከሚለው ቄሣራዊ አገዛዝ ድረስ፤ የሙስና ፖለቲካዊ ዘይቤ መገለጫ ነው፡፡
ሰውም እንደ ሐምሌት፤
“…በምናውቀው ስንሰቃይ፣ የማናውቀውንም ፈርተን
በህሊናችንም ማቅማማት፣ ወኔያችንንም ተሰልበን… መሆን ወይም አለመሆን?...” እያለ ስለበደሉ ማውጠንጠንን ኑሮ ብሎታል፡፡ ወዳጅም ሰው፣ ባላንጣም ሰው፣ ደጋፊም ሰው፣ ተቃዋሚም ሰው፣ የበላይም ሰው፣ የበታችም ሰው ሰው ነው….
“ሰው ይጫኑብህ ግንድ?” ቢሉት፣
ግንድ ከተጫነኝ ሰው ያነሳልኛል፤
ሰው ከተጫነኝ ማን ያነሳልኛል?!” አለ፤ የሚለው የጉራጌ ተረት፤ ይሄንኑ በብርቱ ያፀኸያል!

           አዲስ አድማስ ጋዜጣ በጥቅምት 1 ቀን 2007 ዓ.ም  እትሙ በነፃ አስተያየት አምድ ስር ’’በዲላ ዩኒቨርሲቲ ያዘኑት የተማሪ ወላጆች’’ በሚል ርዕስ ታትሞ የወጣውን ፅሁፍ ተመልክተናል፡፡ ከዚህ ፅሁፍ መገንዘብ እንደቻልነው ዝግጅት ክፍሉ ሊታረሙ ይገባል ብሎ በአስተያየት መልክ ማሳሰቡ በግርድፉ ሲመዘን መልካም ነው ብሎ መውሰድ ይቻል ይሆናል፡፡ ይሁን እንጅ ፅሁፉ የአንድ ወገንን አስተያየት ብቻ ይዞ መውጣቱ አግባብ ነው ብለን አናምንም፡፡ ምንጊዜም ለለውጥ ዝግጁ የሆነ ግለሰብ ወይም ተቋም በገንቢነታቸው የሚሰጡትን አስተያየቶች መውሰድ አለበት፡፡ ተቋማችንም ከዚህ የተለየ አቋም የለውም፡፡
ፀሀፊው በፅሁፉ ካሰፈራቸው አስተያየቶች ለአብነት እየጠቀስን ብንመለከት ‘’ዩኒቨርሲቲው በጣም ሞቃት ስለሆነ ተማሪዎች ’’ሰመራ’’ በማለት በሰየሙት ----’’ የሚለው ገለፃ ከመጠየቅ ስንፈት የመጣ ስህተት ነው፡፡ የዩኒቨርሲቲው ኦዳያኣ ግቢ በተለምዶ ’’ሰመራ’’ ተብሎ ይጠራ የነበረው፣ ከከፍተኛ ሙቀቱ የተነሳ ሳይሆን ግቢው ገና ስራ እንደጀመረ (1999 ዓ.ም) የሰመራ ዩኒቨርሲቲ ተማሪዎችን በጊዜያዊነት (ለአንድ ወሰነ ትምህርት) በዚያ ግቢ በትውስት ተቀብሎ ስላስተማረ ነበር፡፡
ይሁን እንጂ በዚህ ፅሁፍ ላይ ያስተዋልነው ነገር ቢኖር ጋዜጣው (ፀሃፊው) ራሱም እንዳስቀመጠው ለፅሁፉ መነሻ የሆነው መኪና ላይ ያገኛቸው ግለሰቦች መሆናቸውን ይጠቅስና ደግሞ ወደ ታች ወረድ ብሎ በቦታው ተገኝቶ ራሱ ያየው እንደሆነ ያወራል፣ ደግሞ ከዛው ሳይወጣ ስለ ቅበላ ማውራቱን ትቶ አምና ተከሰተ ስለሚለው ነገር ያወራል፡፡ ይህ የሚያሳየን እርስ በርሳቸው የተጣረሱ እና የማጣራት ስራ ያልተሰራባቸው ስህተቶችን ነው፡፡
በፅሁፉ ውስጥ ደረቅ እንጀራ አቅራቢዎች በዱቤ ያቀርቡ እንደነበረና አስተዳደሩ ሲቀየር ገንዘባቸውን ሳይቀበሉ በክስ ሂደት ላይ እንዳሉ ተገልጿል፡፡ ዩኒቨርሲቲው መክሰስም ሆነ መከሰስ የሚችል በአዋጅ የተቋቋመ ህጋዊ ተቋም መሆኑ እንደተጠበቀ ሆኖ፣ የተነሳው ጉዳይ ግን ተጋኖ የሚቀርብ አይደለም፡፡ ዩኒቨርሲቲውም እንጀራ በዱቤ የገዛባቸው ጊዜያት የሉም፡፡
እነዚህ በአብነት የተጠቀሱት ስህተቶች የተከሰቱት ፀሀፊው የዩኒቨርሲቲውን የአስተዳደር አካላት ሳያነጋግር በፅሁፉ ላይ እንደተጠቀሰው በግለሰቦች አስተያየት ላይ ብቻ በራሱ መላምቶች ተመርኩዞ በመፃፉ ነው፡፡ ግለሰቦቹ የተሰማቸውን አስተያየት የመስጠት መብታቸው በህገመንግስታችን የተቀመጠ ዴሞክራሲያዊ መብት በመሆኑ ለምን ሰጡ ብለን ክርክር የምንገጥምበት ጉዳይ አይኖረንም፡፡ በተመሳሳይ ፀሀፊው ዩኒቨርሲቲያችን ላይ ያዩትን (የማየት እድሉ ከነበራቸው) ጠንካራም ሆነ ደካማ ጎን የመፃፍ መብታቸው የተጠበቀ ነው፡፡ ነገር ግን አንድ ፅሁፍ ሲጻፍ በተባራሪ ወሬ ሳይሆን በተጨባጭ ማስረጃ ተመርኩዞ፣ ግራ ቀኙን አይቶ ሁለቱንም ወገን አነጋግሮ፣ ቢቻል በአካል አረጋግጦ መሆን እንዳለበት የጋዜጠኝነት ስነምግባሩም ሆነ የፕሬስ ህጋችን የሚጠይቁት  ግዴታ መሆኑ አያጠራጥርም፡፡ ዝግጅት ክፍሉም ይህንን ሀቅና ሀገራዊ መርህ እንደሚያምንበት እሙን ይሆናል ብለን እንገምታለን፡፡
ከዚህ አንጻር ፅሁፉ የሁለት ወገንን ሀሳብ ያላካተተ መሆኑ ከመጀመሪያው ሚዛናዊነቱን ጥያቄ ውስጥ እንደሚከተው አከራካሪ አይሆንም፡፡ አጠቃላይ ጉዳዮችን ለማብራራት ያህል ግን በእኛ በኩል በያዝነው ዓመት በተቻለ መጠን የተማሪዎቻችንን አቀባበል ስነስርዓት ምቹ በሆነ መንገድ ለማከናወን የተቻለንን ጥረት አድርገናል፡፡ ይህ ማለት ግን ምንም እጥረት የለውም ለማለት አይደለም፡፡ ከዚህ አንፃር ፅሁፉ ላይ የተጠቀሱት በተለይ ደግሞ የተመደበው አንድ አውቶብስ ብቻ ነው የሚለውን ብንወስድ ከእውነት የራቀ አስተያየት ነው፡፡  በእኛ በኩል ያሉንን ተሽከርካሪዎች በተገቢው መንገድ አሰማርተን፣ አሽከርካሪዎች ለምሳ በሚል እንኳን አገልግሎት እንዳያቋርጡ በሽፍት እንዲጠቀሙ አድርገን አገልግሎት ሰጥተናል፡፡ እዚህ ላይ እንደ አስተያየት ሰጪው ግለሰብ ሲታይ፣ ምን አልባት በግለሰቡ አመለካከት ትክክል ሊሆን ይችላል፡፡ ነገር ግን ከህግ አንጻርና እንደ ጋዜጠኛ ሲታይ፣ ግለሰቡ የሰጡትን አስተያየት በመያዝ ከጉዞ ቀርቶም ቢሆን በአካል ተገኝቶ ሁሉንም ጥያቄዎችም ሆነ አስተያየቶች አጣርቶ መሄድ ይጠበቅበት ነበር (ያውም ራሱ ጋዜጠኛው ’’ሰዎቹ ስለዩኒቨርሲቲው የሚናገሩት ፈፅሞ ለማመን የሚያዳግት ነው፤--- ሰዎቹ እንደሚሉት ይሆናል ብዬ ስለማልገምት---’’ እያለ!)፡፡
ከዚህ ጋር በተያያዘም ሌሎች የተሸከርካሪ አማራጮች ማለትም የባጃጅና የጋሪ አገልግሎት ተከለከልን ለሚለው  አስተያየት ከምን አንጻር እንደሆነ ሊመዘን ይገባ ነበር፡፡ ከአሁን በፊት ከነበሩን የተማሪ አቀባበል ስነስርዓቶች በርካታ ልምዶችን ወስደን ለማስተካከል ጥረት አድርገናል፡፡ በፊት ካየናቸው እጥረቶች አንዱ፣ ተማሪዎቻችን በሚገቡበት ወቅት ለከፍተኛ ወጪ መዳረጋቸው እና አልፎ አልፎም የእቃ መጥፋት ሁኔታ ያጋጥማቸው የነበር መሆኑ ነው፡፡ በመሆኑም በዚህ አመት ተቋማችን ከከተማው ፖሊስና ትራፊክ ፅ/ቤት ጋር ቅንጅት በመፍጠር አውቶብሶች ወደ መናሃሪያ ከመሄዳቸው በፊት ወደ ዩኒቨርሲቲያችን እየገቡ የጫኗቸውን ተማሪዎች እንዲያወርዱ በመደረጉ፣ከአሁን በፊት ሲያጋጥሟቸው የነበሩ በርካታ ችግሮች ተቀርፈዋል፡፡ አልፎ አልፎ ወደ ግቢ መግባት ያልቻሉ አውቶብሶች ሲኖሩ ደግሞ ወደ ዩኒቨርሲቲያችን መገንጠያ ሲደርሱ እንዲያቆሙ እየተደረገ፣ በተቋማችን ተሸከርካሪዎች ተማሪዎቻችንን የምናስገባበት አሰራር ነበር ተግባራዊ የተደረገው፡፡ ይህ ደግሞ ተማሪዎቻችን ለወጪ እንዳይዳረጉና ከተለያዩ ተፅዕኖዎች ነፃ እንዲሆኑ አድርጓቸዋል፡፡ ይህ ተግባር ደግሞ የሚያስመሰግን እንጅ የሚያስነቅፍ አልነበረም፡፡ በተቃራኒው በአቀበባል ስነስርዓቱ እረክተው ቢሮ ድረስ ቀርበው ያመሰገኑ ወላጆችም እንደነበሩ ልንገልፅ እንወዳለን፡፡
ሌላው በፅሁፉ የቀረበው ጉዳይ የተቋማችን የአጥርና አጠቃላይ የግንባታዎች ሁኔታ ነው፡፡ ከዚህ አንጻርም ጸሀፊው እንከን የለሽና ሚዛናዊ ይሆን ዘንድ በአካል ማየትና እውነታውን  ከተቋሙ በኩል የማረጋገጥ ግዴታም ነበረበት፡፡ ከላይ እንደገለጽነው በዚህ በኩልም ምንም እንከን የለብንም የሚል አቋም የለንም፡፡ ይሁን እንጂ አሁን ባለው ተጨባጭ ሁኔታ በአጠቃላይ በሀገራችን በሚገኙ የትምህርት ተቋማት ከፍተኛ የግንባታ እንቅስቃሴዎች አሉ፡፡ ይህ መልካም እድል ከገጠማቸው ተቋማት አንዱ የእኛ ዩኒቨርሲቲ ነው፡፡ ይህ ደግሞ ለተቋማችን እና ለአካባቢው ማህበረሰብ ትልቅ ገፀ በረከታችን ነው፡፡
የአጥርም ሆነ ሌሎች ግንባታዎችን በተቻለ ፍጥነት ለማጠናቀቅ ርብርብ እየተደረገ ነው፡፡ ተቋማችን ብቻ ሳይሆን የሚመለከታቸው  ባለድርሻ አካላትም የዞን እና የከተማ አስተዳደሩን ጨምሮ ተገቢውን ትኩረት ሰጥተው በጋራ እየተረባረብን እንገኛለን፡፡
ፀሀፊው ያልተገነዘበው አንዱ ነገር፣ ዩኒቨርሲቲያችን 13 ወር ሙሉ የመማር ማስተማር ስራ የሚያከናውንና በ2006 ዓ.ም የክረምት መርሃ ግብርም በርካታ ተማሪዎችን ተቀብሎ እያስተማረ የቆየ ሲሆን የክረምት ተማሪዎችን ከሸኘ በኋላም መደበኛ ተማሪዎችን ለመቀበል ቅድመ ዝግጅት አድርጓል፡፡ ይህም በመሆኑ ምንም አይነት ተዘግቶ የከረመና ፀሀፊው በከፍተኛ ግነት ነገሩኝ ያላቸው ግለሰቦች እንደገለፁት፣ በአቧራ ተሞልቶ ተባይ አስከሚያፈራ የደረሰ መኝታ ቤትና የተበለሻሹ ግብዓቶች የመኖራቸው ጉዳይም ትክክል አለመሆኑን ታዝበናል፡፡
ይልቁንም ለእያንዳንዱ የተማሪ መኝታ ክፍል ህንጻዎች የጽዳት ባለሙያዎችና ተቆጣጣሪዎች  ያሉበት፣ ተማሪዎቹም ከመግባታቸው በፊት አስፈላጊውን ሁሉ ዝግጅት በማከናወን ተማሪዎቻችንን የተቀበልን መሆናችን ልብ እንዲባል እንፈልጋለን፡፡
ተማሪዎች እንደማንኛውም የተሻለ ምቾት ሊመርጥ እንደሚችል ግለሰብ ሁሉ የታሸገ ወይም የቀዘቀዘ ውሃ ገዝተው ሊጠቀሙ ይችላሉ፡፡ ይህ እውነታ በከፍተኛ ሁኔታ ተኳሽቶ፣ ምንም አይነት ውሃ በግቢ ውስጥ እንደሌለና ተማሪዎችም እግራቸውን እንኳን የሚታጠቡበት አጥተው እንደተቸገሩ አድርጎ ማቅረቡ፣ ከአንድ ጋዜጠኛ የማይጠበቅ ስነምግባር ነው፡፡ በነገራችን ላይ በቅርቡ ለሁሉም ህንጻዎች  የሚዳረስ፣ ከዚህ በፊት ከሚጠቀሙበት የተሻለ መጠንና ጥራት ያለው ውሃ ተገኝቶ፣ የሙከራ ስርጭት ተደርጎ፣ በየህንጻው ላይ ያሉ የመፀዳጃ ቤቶች ክፍት እንደሚሆኑ እየገለፅን፣ ጸሀፊው ሰባት መቶ ሜትር ሄደው ጫካ ይፀዳዳሉ ብሎ ላቀረበው ሃሳብ፣ ከህንፃዎች ውጪ ጊዜያዊ መፀዳጃ ቤቶችን በመገልገል ላይ ያሉ በመሆኑ የፀሀፊው ሃሳብ እኛን አይገልፀንም፡፡ በአካል ተገኝቶ ለማየት እንደሚቻለው ሁሉ በኦዳያኣ ግቢ (በፀሐፊው አገላለፅ ’’ሰመራ’’ ግቢ) ውስጥ ተማሪዎችም እንደሚመሰክሩት፣ጭቃ በከፍተኛ ሁኔታ ቀንሷል፡፡ መኝታ ቤቶችን ከመንገድ፣ መማሪያ ክፍሎችን ከመንገድና እርስ በርሳቸው የሚያገናኙ የድንጋይ ንጣፍ መንገዶች (ኮብል ስቶን መንገድ) ተሰርተዋል፡፡ ከከተማው አስተዳደር ጋር ተያይዞም ፅሁፉ ላይ የተቀመጠው ጉዳይም ሚዛናዊነቱን የጠበቀ አይደለም፡፡ ከተማ አስተዳደሩም ሆነ የከተማው ማህበረሰብ ዩኒቨርሲቲውን አይፈልገውም የሚለው ጫፍ የወጣ ዘገባ ማስቀመጥም ከግዴለሽነት የሚመነጭ ካልሆነ በስተቀር አንድም የከተማው ማህበረሰብ ተጠይቆ አልፈልግም ባላለበት ሁኔታ መንገደኞችን አነጋግሮ ጥርጣሬ አለኝ ብሎ ማስቀመጥ፣ አጠቃላይ ማህበረሰቡን ካለመረዳት የሚመነጭ በመሆኑ ከህግም አንጻር ሲታይ ተገቢ ያልሆነና ሊያስጠይቅ የሚችል ጉዳይ እንደሚሆን ይሰማናል፡፡
የአካባቢው መስተዳድርና ማህበረሰብም ከዩኒቨርሲቲው ተጠቃሚ እንደሆኑ አጥብቀው የሚያምኑና  የቅርብ ክትትልና ድጋፍ እያደረጉ እንደሆነ በአፅንኦት ሊሰመርበት ይገባል፡፡ ነገር ግን ከአፍራሽነት የሚመነጭ፣ ተቋሙንና ማህበረሰቡን ለማቃረን የማለም እቅድ ካልሆነ በስተቀር ይህንን በአካል ቀርቦ ተቋሙ ለማህበረሰቡ እየሰጠ ያለውን ድጋፍና ተተግብረውም የመጡትን ለውጦች አይቶ በመገምገም ሚዛናዊ ፅሁፍ መፃፍ ይቻል እንደነበረ ግልፅ ነው፡፡ በአጠቃላይ ሲታይ ዩኒቨርሲያችን የሀገራችን ዩኒቨርሲቲዎች ሁሉ እንደሚያደርጉት በግንባታም ይሁን በአጠቃላይ የትምህርት ስራ እንቅስቃሴ ራዕዩን ለማሳካት በተሻለ እንቅስቃሴ ላይ እንደሆነ እንዲታወቅና በዚህ የልማት እንቅስቃሴ ወቅት የሚከሰቱ መጠነኛ ችግሮችን እያጎላን ልማታችንን ከማደናቀፍ በዘለለ ጠንካራ ጎኑንም በማየትና መጠነኛ ችግሮችን በጋራና በንቃት እየቀረፍን መጓዝ እንዳለብን የጋራ ስሜት መያዝ የተቋማችን ብቻ ሳይሆን የሚዲያዎች ሚናም እንደሆነ ስለምናምን፣በእናንተ በኩል ይህ ሚዛናዊነቱን ያልጠበቀ ፅሁፍ ቢቻል ሁሉንም ጉዳዮች ከሚመለከታቸው የተቋማችን ኃላፊዎች ጋር በመገናኘትና ሁሉንም ተግባር በአካል በመጎብኘት እውነቱን እንድታረጋግጡ እንጋብዛለን፡፡ከአዘጋጁ፡ ዩኒቨርሲቲው ከላይ እንደገለጸው የተማሪ ቤተሰቦችን ቅሬታ ብቻ ሳይሆን የዩኒቨርሲቲውን አካል ምላሽ ማካተት ተገቢ እንደነበር እናምናለን፡፡ ሆኖም በአካል ተገኝተን ሁኔታውን ለማየት በቂ ጊዜ ስላልነበረን ጋዜጣውን ወደ ማተሚያ ቤት እስከላክንበት የመጨረሻዋ ደቂቃ ድረስ በሁለት የዩኒቨርሲቲው ስልኮች በመደወል ምላሽ የሚሰጠን አካል ለማግኘት የጣርን ቢሆንም ስልኩን የሚያነሳ ባለመኖሩ ሙከራችን ሳይሳካ ቀርቷል፡፡ እንዲያም ሆኖ ዲላ ዩኒቨርሲቲ በዚህ ሳምንት ከተማሪ ቤተሰቦች ለተሰነዘረው ቅሬታ ከላይ የቀረበውን ምላሽ በጽሁፍ ስለላከልን ከልብ እናመሰግናለን፡፡




“ኢቦላ ኢትዮጵያ ውስጥ ገብቷል የሚባለው ሃሰት ነው”

የኢትዮጵያ መንግሥት የፀጥታ ክፍሉ ጠንካራና ህብረተሰቡን ያማከለ በመሆኑ ከአልሸባብም ሆነ በሌሎች ሀገሮች ከሚደገፉ አሸባሪዎች ሊደርስ የሚችል ጥቃት እንደማይኖር የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር አረጋገጠ፡፡
ሰሞኑን የአሜሪካ የውጭ ጉዳይ መስሪያ ቤት አዲስ አበባ በሚገኘው ኤምባሲው አማካኝነት በቦሌ አካባቢ አልሸባብ ጥቃት ሊፈፅም እንደሚችል መረጃው ደርሶኛል በማለት ዜጐቹ በአካባቢው ሲንቀሳቀሱ ጥንቃቄ እንዲያደርጉ በድረገፁ መልእክት ማስተላለፉ የሚታወስ ሲሆን በኢትዮጵያ የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር የአሜሪካ ጉዳይ ዳይሬክተር አምባሳደር ታዬ አፅቀስላሴ በበኩላቸው፤ “የሀገሪቱ ፀጥታ የተጠናከረ ነው፤ የዲፕሎማቲክ ማህበረሰቡ ስጋት አይግባው” ብለዋል፡፡
የሀገሪቱን ደህንነት የምንጠብቀው በተለያዩ ጊዜያት በሚሰጡ የጥቃት ማስጠንቀቂያዎች አይደለም ያሉት አምባሳደሩ፤ የፀጥታ ሃይሉ የህብረተሰቡን ደህንነት የመጠበቅ ሃላፊነቱን ለመወጣት እለት ከእለት በጥንካሬ እየሰራ ነው ብለዋል፡፡
በሌላ በኩል በትናንትናው እለት የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር መስሪያ ቤት ለዲፕሎማቶችና ለአለማቀፍ ድርጅቶች ተወካዮች በሰጠው መግለጫ፤ ኢትዮጵያ ውስጥ የኢቦላ ታማሚ እንደሌለ አረጋግጧል፡፡
ሰሞኑን በማህበራዊ ድረ-ገፆች ኢትዮጵያ ውስጥ በጥቁር አንበሳና በቅዱስ ያሬድ ሆስፒታል የኢቦላ ታካሚዎች አሉ በሚል የተሰራጩ መልእክቶች ከእውነት የራቁ መሆናቸውን ሚኒስቴር መስሪያ ቤቱ አስታውቋል፡፡
ከተለያዩ ወገኖች የሚቀርቡ ጥቆማዎች በስልክ መስመር 8335 ላይ እያስተናገደ መሆኑን የጠቆመው መስሪያ ቤቱ፤ የኢቦላ ታማሚ ኢትዮጵያ ውስጥ ቢገኝ እንደማይደበቅና ሀገሪቱ ለጉዳዩ ትኩረት ሰጥታ እየሰራች እንደሆነ ገልጿል፡፡
በሽታው ሀገር ውስጥ ቢገባ እንኳን በብቃት ምላሽ ለመስጠት ጠንካራ ዝግጅት መደረጉንም ጠቁሟል፡፡

        ፕሮፌሰር መስፍን ወልደ ማርያም ተቀማጭነቱ በአውስትራሊያ የሆነው ‘ዲሞክራሲ ፎር ኢትዮጵያ ሰፖርት ግሩፕ’ የተሰኘ ቡድን ያዘጋጀውን የእድሜ ዘመን ስኬት ሽልማት ለመቀበል ሰሞኑን ወደ አውስትራሊያ መሄዳቸውን ምንጮቻችን ገለጹ፡፡
ፕሮፌሰር መስፍን ወልደ ማርያም በአገሪቱ ሁሉን አቀፍ ሰላምና መረጋጋት እንዲሰፍን ለማስቻል ለረጅም አመታት ትልቅ አስተዋጽኦ አበርክተዋል ያለው ቡድኑ፣ ላበረከቱት አስተዋጽኦ እውቅና ለመስጠት በማሰብ ሽልማቱን  እንዳበረከተላቸው አስታውቋል፡፡
ፕሮፌሰሩ ሽልማቱን ከመቀበላቸው በተጨማሪ፣ ከነገ ጀምሮ በሚልቦርን፣ በሲድኒ፣ በብሪስባኔና በሌሎች የአውስትራሊያ ከተሞች ከሚኖሩ ኢትዮጵያውያን ጋር በአገራዊ ጉዳዮች ዙሪያ ውይይት እንደሚያደርጉ ይጠበቃል፡፡
በሰብዓዊ መብቶች፣ በታሪክ፣ በጂኦግራፊና በልማት ጉዳዮች ዙሪያ የሚያጠነጥኑ የተለያዩ መጽሃፍትንና የጥናት ወረቀቶችን የጻፉትና ለረጅም አመታት በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ በመምህርነትና በተለያዩ የመንግስት ድርጅቶች ያገለገሉ ፕ/ር መስፍን፣ ከኢትዮጵያ የሰብዓዊ መብቶች ጉባኤ መስራቾች አንዱ ሲሆኑ፣ ለተለያዩ የተቃዋሚ የፖለቲካ ፓርቲዎች አማካሪ ሆነው ሲሰሩ መቆየታቸው ይታወቃል፡፡