Administrator

Administrator

           የኬንያው ፕሬዚዳንት ኡሁሩ ኬንያታ ከሰባት አመታት በፊት በኬንያ የተካሄደውን ምርጫ ተከትሎ በአገሪቱ ከተቀሰቀሰውና ከ1ሺህ 200 በላይ ዜጎችን ለህልፈተ ህይወት፣ 600 ሺህ ያህሉን ደግሞ ለመፈናቀል ከዳረገው የእርስ በርስ ግጭት ጋር በተያያዘ በአለማቀፉ የወንጀለኞች ፍ/ቤት የተመሰረተባቸውን ክስ ባለፈው ረቡዕ በፍ/ቤቱ ቀርበው አደመጡ፡፡
በስልጣን ላይ እያሉ በአለማቀፉ ፍርድ ቤት የቀረበባቸውን ክስ ለማድመጥ በፈቃደኝነት የተገኙ የመጀመሪያው ፕሬዚዳንት የሆኑት ኡሁሩ ኬንያታ፣ ዘ ሄግ በሚገኘው ፍ/ቤት በተዘጋጀው የቅድመ ፍርድ ሂደት ውይይት ላይ ተገኝተው የተመሰረቱባቸውን አምስት የወንጀል ክሶች ያደመጡ ሲሆን፣ ወንጀሎቹን አለመፈጸማቸውን ለፍርድ ቤቱ እንደገለጹ ቢቢሲ ዘግቧል፡፡
“የተመሰረቱብኝ ክሶች ከፖለቲካዊ ጥቅም ጋር የተያያዙ ናቸው፡፡ ክሶቹ ውድቅ ሊደረጉ ይገባል” ብለዋል ምክትላቸውን ዊሊያም ሩቶን በቦታቸው ወክለው፣ ክሱን ለማድመጥ ወደ ፍርድ ቤቱ የሄዱት ኬንያታ በሰጡት ምላሽ፡፡
በ2007 የኬንያ የምርጫ ውዝግብን ተከትሎ በአገሪቱ በተከሰተው ግጭት ውስጥ እጃቸው አለበት፣ ሰብዓዊ መብቶችን በሚጥሱ የወንጀል ተግባራት ላይ ተሳትፈዋል በሚል በቀረቡባቸው አምስት ክሶች፣ የሚሊሺያ ወታደሮችን በገንዘብ በመደገፍ ለጥቃት አነሳስተዋል፤ ጉዳያቸው በመደበኛ ፍርድ ሂደት ይታይ አይታይ የሚለው  ሐሙስ የሚወሰን ይሆናል፡፡በዕለቱ አቃቤ ህግ፤ የኬንያ መንግስት በፕሬዚዳንቱ ላይ ከተመሰረተው ክስ ጋር ተያያዥነት ያላቸው ቁልፍ ማስረጃዎችን ለመስጠት ፈቃደኛ አልሆነም በሚል ቢወነጅልም፣ ኬንያዊው ጠበቃ ጊቱ ሙጋይ ግን  ውንጀላውን አልተቀበሉትም፡፡ ፍርድ ቤቱ በቂ ማስረጃ ካላገኘ፣ ክሶቹ ውድቅ ሊደረጉ ይገባል ሲሉም ተናግረዋል፡፡

አቃቤ ህግ በበኩሉ፤ ወንጀሎቹ  በፕሬዚዳንቱ መፈጸማቸውን የሚያረጋግጡ የስልክ ማስረጃዎችና ዘጠኝ ምስክሮች እንዳሉት አስታውቋል፡፡ፍርድ ቤቱ በኡሁሩ ኬንያታ ላይ የተመሰረተውን ክስ ውድቅ ማድረጉን አልያም የፍርድ ሂደቱ መቀጠል እንዳለበት ሰሞኑን ውሳኔ ይሰጣል ተብሎ ይጠበቃል፡፡
በአፍሪካ በስልጣን ላይ እያሉ በአለማቀፉ የወንጀለኞች ፍርድ ቤት ክስ የተመሰረተባቸው ሌላው መሪ፣ የሱዳኑ ኦማር አልበሽር እንደሆኑ ያስታወሰው ዘገባው፤ በዳርፉር በተከሰቱ የጦርነት ወንጀሎች ተከስሰው  ፍርድ ቤቱ ያወጣባቸውን የእስር ትዕዛዝ አልቀበልም ማለታቸውን ጠቁሟል፡፡በፍርድ ቤቱ የነበራቸውን ቆይታ አጠናቀው ባለፈው ሃሙስ ወደ አገራቸው የተመለሱት ኡሁሩ ኬንያታ፣ ናይሮቢ በሚገኘው አየር ማረፊያ ሲደርሱ በባህላዊ ጭፈራና የወታደራዊ ማርሽ የታጀበ ደማቅ አቀባበል ተደርጎላቸዋል፡፡ ከአየር ማረፊያ እስከተማዋ ማዕከላዊ አደባባይ በሺዎች የሚቆጠሩ ደጋፊዎቻቸውም ለፕሬዚዳንታቸው ደማቅ አቀባበል አድርገዋል፡፡
“አንድ ነን!... ኬንያ የተረጋጋች አገር ስለሆነች ምንም የሚያሰጋ ነገር የለም!” ብለዋል ኬንያታ ለህዝቡ ባሰሙት አጭር ንግግር፡፡

  • ውጤት ያልቀናቸው ባሬቶ፤ በሥራቸውም ውጣ ውረድ በዝቶባቸዋል፡፡
  • ምድብ 2 ለማለፍ አልጄርያ እና ማሊ የተሻለ እድል ይዘዋል፡፡
  • ዋልያዎቹና ንስሮቹ ሲነፃፀሩ፤ የኃይል ሚዛኑ ወደ ማሊ  ያጋድላል፡፡

    ዩሱፍ ሳላህ
30 ዓመቱ ነው
ትውልዱ በስዊድን ሶላና ነው፡፡
የግራ ክንፍ መስመር ላይ ይጫወታል፡
አሁን በስዊድኑ ክለብ አይኬ ሳይረስ     ይጫወታል፡፡
ከ2012 እኤአ ጀምሮ ለኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን 9 ጨዋታዎችን አድርጎ     1 ጎል አስመዝግቧል፡፡
በዝውውር ገበያው ያለው የዋጋ ግምት 150ሺ ዩሮ ነው፡፡


አሚን አስካር
29 ዓመቱ ነው፡፡
ትውልዱ በሃረር ኢትዮጵያ ውስጥ ነው፡፡
የክንፍ መስመር ላይ ይጫወታል፡፡
ከ2012 እኤአ ጀምሮ ብራነር በተባለ     የኖርዌይ ክለብ እየተጫወተ ነው፡፡
በዛሬው ጨዋታ ለኢትዮጵያ ለመጀመርያ ጊዜ የሚሰለፍ ይሆናል፡፡
በዝውውር ገበያው ያለው የዋጋ ግምት 1 ሚሊዮን ዩሮ ነው፡፡

ዋሊድ አታ
28 ዓመቱ ነው፡፡
ትውልዱ በሳውዲ አረቢያ ሪያድ ነው፡፡
የመሃል ተከላካይ ሆኖ ይሰለፋል፡፡
በ2014 እኤአ ላይ ቢኬ ሃከን በተባለ     ክለብ እየተጫወተ ነው፡፡
ከ2008 እሰከ 2009 እኤአ በስዊድን ሀ21 ብሄራዊ ቡድን ሶስት ጨዋታዎች አድርጓል፡፡
በዝውውር ገበያው ያለው የዋጋ     


ለ31 ዓመታት ያለተሳትፎ የራቀበትን አህጉራዊ ውድድር ከ1 ዓመት በፊት ደቡብ አፍሪካ ባስተናገደችው 29ኛው  የአፍሪካ ንጫ በመሳተፍ ታሪኩን የቀየረው፤ የኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን ይህን ስኬት ለመድገም አጣብቂኝ ውስጥ ነው፡፡ አንዳንድ ስፖርት ቤተሰቦች ኢትዮጵያ በቅርብ ዓመታት ውስጥ ለአፍሪካ ዋንጫ ተሳትፎ የምትበቃው በውድድሩ አዘጋጅነት ብቻ መሆኑን ይገልፃሉ፡፡ በ2015 እኤአ ላይ በሞሮኮ ለሚካሄደው 31ኛው የአፍሪካ ዋንጫ ለማለፍ በመላው አህጉሪቱ የሚደረገው የምድብ ማጣርያ በዚህ ሰሞን አጋማሹ ላይ ይደርሳል፡፡ ከትናንት ጀምሮ በሚካሄዱት የ3ኛው ዙር የምድብ ማጣርያ ጨዋታዎች ኢትዮጵያን ጨምሮ  10 ብሄራዊ ቡድኖች በፉክክሩ ለመቆየት ይፋለማሉ፡፡ የሰባት ግዜ ሻምፒዮኗን ግብፅን ጨምሮ ኢትዮጵያ፤ ሌሶቶ፤ቦትስዋና፤ ቶጎ፤ ሴራልዮን፤ አንጎላ  እና ሱዳን በዚህ ዙር ተጋጣሚዎቻቸውን ማሸነፍ ብቸኛ አማራጭ ይሆንባቸዋል፡፡
ማርያኖ ባሬቶና ውጣውረዳቸውፖርቱጋላዊው ማርያኖ ባሬቶ በብሄራዊ ቡድን ዋና አሰልጣኝነት የቆዩባቸው ያለፉት 6 ወራት ውጣውረዶች የበዙባቸው ነበሩ፡፡ ከአሰልጣኝ ሰውነት ቢሻው ስንብት በኋላም የዋልያዎቹ ውጤታማነት እየወረደ መጥቷል

የኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌደሬሽን በተከተለው ግልፅነት የጎደለው ቅጥራቸው በርካታ የስፖርት ቤተሰብ ደስተኛ አልነበረም፡፡ ያም ሆኖ ፌደሬሽኑ ብሄራዊ ቡድኑን ለአፍሪካ ዋንጫ የሚያሳልፉ እና በወጣቶች ላይለማከናውናቸው ስራዎች መሰረታዊ ድጋፍ በመስጠት ያግዙኛል ያላቸውን ፖርቱጋላዊ አሰልጣኝ ማርያኖ ባሬቶ በ2 ዓመት የቅጥር ኮንትራት ኃላፊነቱን ሰጥቷቸዋል፡፡ በወር 18 ሺ ዶላር የተጣራ ደሞዝ ይከፍላቸዋል፡፡ ባለፉት 6 ወራት ፌደሬሽኑ ለእኝህ አሰልጣኝ ከሌሎች ጥቅማ ጥቅሞች ውጭ እስከ 109ሺ ዶላር በደሞዝ ብቻ ከፍሏል 2.16 ሚሊዮን ብር አካባቢ ማለት ነው፡፡ ይሁንና የኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን በማርያኖ ባሬቶ ሃላፊነት ከወደቀ በኋላ ውጤት ርቆታል፡፡ እስካሁንም ነጥብ ማስመዝገብ  ልተሳካለትም፡፡ ማርያኖ ባሬቶ ከማሊ ጋር የሚገናኙበት የዛሬው ጨዋታ በአዲስ አበባ ስታድዬም ተመልካች ፊት ለሁለተኛ ጊዜ የሚያደርጉት የነጥብ ጨዋታ ነው፡፡ ብሄራዊ ቡድኑ በዚህ ወሳኝ ጨዋታ ማሸነፍ ያለው ብቸኛ አማራጭ ሲሆን ከተሸነፈ ግን የአሰልጣኙን  ቆይታ ከፍተኛ ውጥረት ውስጥ ይከተዋል፡፡ የ57 ዓመቱ ማርያኖ ባሬቶ በብሄራዊ ቡድን አሰልጣኝነታቸው

የቆዩባቸው 190 ቀናቶች ምንም ነጥብ አለማስመዝገባቸው የሚያሳስብ ነው፡፡ ለዚህም የቀድሞው አሰልጣኝ ሰውነት ቢሻው በሃላፊነቱ በቆዩባቸው 830 ቀናት የነበራቸው ስኬት ማስረጃ ይሆናል፡፡ በዋልያዎቹ ዋና አሰልጣኝነት 17 ጨዋታዎች ያደረጉት ሰውነት ቢሻው፣ በአንድ ጨዋታ በአማካይ 1.35 ነጥብ ይሰበስቡ ነበር፡፡ በሜዳቸው የሚያደርጓቸውን ጨዋታዎች በማሸነፍም ከሜዳ ውጭ ደግሞ ነጥብ በመጋራት እና በማሸነፍ ሰውነት ቢሻው የተሻሉ ነበሩ፡፡በእርግጥ ዋና አሰልጣኝ ማርያኖ ባሬቶ የብሄራዊ ቡድኑን የአፍሪካ ዋንጫ ማጣርያ ተሳትፎ በውጤታማ ጉዞ ለመጀመር ቢሳናቸውም በቆይታቸው አንዳንድ ምስጉን ተግባራትን አከናውነዋል፡፡ የምድብ ማጣርያውን ከመጀመራቸው በፊት ከአንጎላ ጋር የወዳጅነት ጨዋታ እንዲካሄድ ማስቻላቸው የመጀመርያው ውጤት ነው፡፡ ከዚያም ዋልያዎቹን ለ2 ሳምንት  ወደ ብራዚል በመውሰድ ልዩ አይነት ዝግጅት እንዲሰራ አድርገዋል፡፡ የብሄራዊ ቡድኑን ልምድ እና ብራንድ በማሳደግ ስኬታማ ነበር፡፡ በሌላ በኩል አንዳንድ ወጣት ተጨዋቾችን ወደ ቡድኑ በመቀላቀል ያሳዩት ቁርጠኛነት ተደንቆላቸዋል፡፡ ከላይ ከተዘረዘሩት ውጤታማ ተግባራት ዋና አሰልጣኙ በሃላፊነቱ በቆዩባቸው ባለፉት ስድስት ወራት በተለያዩ ጉዳዮች ከተጨዋቾች እና ከፌደሬሽኑ ያስቻላቸው ሁኔታዎች አሉታዊ ተፅእኖ ፈጥሮባቸዋል፡፡ ይህንኑ በተመለከተም ማርያኖ ባሬቶ በሁለቱ የምድብ ማጣርያ ጨዋታዎች ሽንፈቶች ከገጠማቸው በኋላ በተለይ ለሱፕር ስፖርት እና ለአገር ውስጥ መገናኛ ብዙሃናት ውጤታማ ስራ ላለማከናወን ምክንያቶች ናቸው ባሏቸው ጉዳዮች ላይ በተደጋጋሚ ቅሬታቸውን ሲገልፁ እና ሲተቹ ቆይተዋል፡፡ዋና አሰልጣኙ  በዝግጅታቸው የብሄራዊ ቡድን ተጨዋቾች የፕሮፌሽናሊዝም ደረጃ አላረካቸውም ነበር፡፡ በብዙዎቹ ተጨዋቾች የስራ ዲስፕሊን ላይ ቅሬታቸውን በተደጋጋሚ ይናገሩ ነበር፡፡ ከዚሁ ጋር አያይዘውም ብዙዎቹ የብሄራዊ ቡድን ተጨዋቾች ከስዊድን ከመጣው ዩሱፍ ሳላህ ብዙ መማር እንዳለባቸውም ሲመከሩ ሰንብተዋል፡፡ በሌላ በኩል አሰልጣኙ ከ2 ሳምንት በፊት ለሱፕር ስፖርት በሰጡት ማብራርያ ቡድናቸው በተጨዋቾች ጉዳት ክፍተት እንደበዛበት ተናግረው ነበር፡፡ በዚህም በአበበ ቢቂላ ስታድዬም በአርቴፊሻል ሳር ላይ

የተሰራው  ልምምድ ሰበብ በመሆኑ ደስተኛ አይደለሁም በማለት ወቅሰዋል፡፡  በወቅቱ በአፍሪካ ዋንጫው 3ኛ የምድብ ማጣርያ ጨዋታ ከማሊ ጋር አዲስ አበባ ላይ ከመደረጉ በፊት የወዳጅነት ጨዋታ ተገኝቶ አቋም ለመፈተሽ አለመቻሉንም ክፉኛ አማርረዋል፡፡ በተያያዘ የማሊን ቡድን ለመገምገም የሚያስችል የጨዋታ ቪድዮዎችን በፌደሬሽኑም ሆነ በግል ጥረታቸው ለማግኘት ፈልገውም ስላልሆነላቸው ቅሬታ ነበራቸው፡፡ በተጨማሪም በአንዳንድ የመጫወቻ ቦታዎች ተጨዋቾችን ማጣታቸውን ሲነቅፉም ብዙዎቹ የኢትዮጵያ ክለቦች የውጭ አገር ተጨዋቾችን በመቅጠራቸው ተተኪ ለማግኘት እንቅፋት እንደሆነባቸውም በመግለፅ ነበር፡፡ለአልጄሪያና ማሊ የተሻለ ዕድል የሚያሳዩት የምድብ 2 ሁኔታዎች
ዛሬ ከማሊ ጋር በአዲስ አበባ ስታድዬም  ለ31ኛው የአፍሪካ ዋንጫ ከሚደረገው የምድብ ማጣርያ 3ኛ ዙር ጨዋታ በፊት ኢትዮጵያ በምትገኝበት ምድብ ሁለት ያለምንም ነጥብ በ2 የግብ እዳ የመጨረሻ ደረጃ ላይ ናት፡፡ አልጄርያ በ6 ነጥብ እና በ2 የግብ ክፍያዎች መሪነቱን ስትይዝ፤ ማሊ በ3 ነጥብ እና በ1 የግብ ክፍያ ሁለተኛ እንዲሁም ማላዊ በ3 ነጥብ ሶስተኛ ደረጃ ላይ ናቸው፡፡ በምድቡ የ3ኛ እና የ4ኛ ዙር ማጣርያ ጨዋታዎች ኢትዮጵያ እና ማሊ በአዲስ አበባ እና በባማኮ፤ እንዲሁም በሌላ የምድብ 2 ጨዋታ ማላዊ እና አልጄርያ 
በብላንታየርና አልጀርስ ከተሞች የደርሶ መልስ ጨዋታዎቻቸውን ያደርጋሉ፡፡ኢትዮጵያ በምድብ ማጣርያው ሁለት ጨዋታዎች በሜዳዋ ላይ በአልጄርያ 2ለ1 ከተሸነፈች በኋላ  በሁለተኛው ዙር ጨዋታ ከሜዳዋ ውጭ በማላዊ 3ለ2 ተረታለች፡፡ የዛሬ ተጋጣሚዋ የሆነችው የምእራብ አፍሪካዋ ማሊ በአንፃሩ  በመጀመርያ ጨዋታዋ ማላዊን 2ለ0 ብትረታም በሁለተኛው ጨዋታ በአልጄርያ 1ለ0 ተሸንፋ በምድብ ሁለት ሁለተኛ ደረጃን ይዛለች፡፡ የኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን በአልጄርያ እና በማላዊ ከደረሱበት ሽንፈቶች በኋላ ዋና አሰልጣኝ ማርያኖ ባሬቶ ከማሊ ጋር ለሚደረገው ወሳኝ የ3ኛ ዙር ማጣርያ ጨዋታቸው  23 ተጨዋቾችን በመጥራት  ከ10 ቀናት በላይ አሰርተዋል፡፡ ቡድኑ ባለፈው ማክሰኞ ብቸኛውን የአቋም መፈተሻ ግጥሚያ ያደረገው ከኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ጋር ነው፡፡ በዛሬው ጨዋታ ለዋልያዎቹ ከፍተኛ ክፍተት የሆነው የሳላዲን ሰኢድ አለመኖር ነው፡፡ በግብፅ ፕሪሚዬር ሊግ የመጀመርያውን የሻምፒዮናነት ክብር ለማግኘት የበቃው ሳላዲን ሰኢድ ለማሊው ጨዋታ አለመድረሱን በተመለከተ ይቅርታ ጠይቋል፡፡ አልሃሊ ከዛማሌክ ባደረጉት ጨዋታ ጉዳት የደረሰብት ሳላ እስከ ስድስት ሳምንት ከሜዳ መራቅ የብሄራዊ ቡድኑን አቅም ያዛባዋል፡፡  በውጭ አገር ክለቦች ይጫወቱ የነበሩት ያሉት ዩሱፍ ሳላህ፤ አሚን አስካር እና ዋሊድ አታ ብሄራዊ ቡድኑን በመቀላቀል ያለፉትን አምስት ቀናት ማርያም የሰሩት ይህን

ክፍተት ለመሸፈን ነው፡፡ በሳምንቱ አጋማሽ ላይ ደግሞ አራት ተጫዋቾች አሰልጣኙም መቀነሳቸው አወያይቷል
የተቀነሱት አዳነ ግርማ፣ አሉላ ግርማ፣ አንተነህ ተስፋዬ እና ግብ ጠባቂው ዮሃንስ በዛብህ ናቸው፡፡ እንደ ሱፐር ስፖርት ትንታኔ በዛሬው የኢትዮጵያና ማላዊ ጨዋታ በአማካይ መስመር ናትናኤል ዘለቀና ሽመልስ በቀለ ከጣሊያኑ የኤስ ሮማ ክለብ ተጨዋች ከሆነው ሰይዱ ኪዬቴ ጋር ይጋፈጣሉ፡፡ የዎልቨርሃምተኑ የክንፍ መስመር

ተጨዋች ባካሪ ሳኮ እና የፈርንሳዩ  ክለብ ቦርዶክስ አጥቂ የሆነው ቺዬክ ዲያቤቴ ለኢትዮጵያ ተከላካይ መስመር ፈተና እንደሚሆኑም ዘገባው አመልክቷል፡፡ ኢትዮጵያ በአጥቂ መስመር ስኬታማውን ሳላዲን ሰኢድ አለማሰለፏ እንደሚጎዳት የገለፀው ሱፕር ስፖርት፤ በግብፅ ክለብ የሚጫወተው ኡመድ ኡክሪ እና በደቡብ አፍሪካ ክለብ የሚጫወተው ጌታነህ ከበደ የማሊ ተከላካይ መስመር ለማስከፈት ከፍተኛ ፈተና ይጠብቃቸዋል ብሏል፡፡  በሌላ በኩል የበረሃዎቹ ቀበሮዎች ከማላዊ ጋር በሚያደርጓቸው የደርሶ መልስ ጨዋታዎች የምድብ 2 መሪነታቸከማሊ ጋር ያለውን ክፍተት ለማጥጭበብ በተለይ በሜዳቸው የሚደረገው ጨዋታ ወሳኝ ነው ዋልያዎቹ ከንስሮቹ ኢትዮጵያና ማሊ በታሪክ ለመጀመርያ ጊዜ ዛሬ በአዲስ አበባ ስታድዬም መገናኘታቸው ውጤቱን ለመገመት
አዳጋች አድርጎታል፡፡ ጎልዶትኮም አንባቢዎቹን በማሳተፍ በሰራው ትንበያ 67 በመቶ የማሸነፍ እድል የሰጠው ለኢትዮጵያ ሲሆን ማሊ 33 በመቶ ግምት ወስዳለች፡፡ የኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን ከማሊ ጋር በሚያደርጋቸው ሁለት የደርሶ መልስ ጨዋታዎች  4 እና ከዚያም በላይ ነጥብ ካስመዘገበ በማጣርያው የሚኖረው ተስፋ

ያንሰራራል፡፡ በ3ኛው የምድብ ማጣርያ ጨዋታ በተለይ በዛሬው መሸነፍ ማለት ግን የሞሮኮን 31ኛው የአፍሪካ ዋንጫ መሳተፍ ህልም አበቃለት ማለት ነው፡፡ ኢትዮጵያና ማሊ ሁለቱን የደርሶ መልስ ጨዋታዎችን በአራት ቀናት ልዩነት ያደርጋሉ፡፡ ይህ ሁኔታ ደግሞ ልምድ በሚያነስው የኢትዮጵያ ቡድን አቋም ላይ ተፅእኖ ይፈጥራል፡፡የምድብ ማጣርያው ሲጀመር 23 ተጨዋቾችን ያሰባሰበው የኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን በትራንስፈር ማርኬት ድረገፅ የወጣለት የተጨዋቾች ዝውውር ገበያ የዋጋ ግምቱ 725ሺ ዩሮ ነበር፡፡ ዋሊድ አታ እና አሚን አስካር ሰሞኑን ቡድኑን ከተቀላቀሉ በኋላ ግን ይህ ዋጋ ወደ 2.3 ሚሊዮን ዩሮ ከፍ ብሏል፡፡ የኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን አማካይ እድሜው 26.2 ዓመት ሲሆን በስብስቡ ያካተታቸው በውጭ አገር የሚጫወቱ ፕሮፌሽናሎች ብዛት 9 ደርሷል፡፡ ንስሮቹ በሚል ቅፅል ስም የሚጠራው የማሊ ቡድን ባለፉት ሁለት የአፍሪካ ዋንጫዎች ሶስተኛ ደረጃዎችን አከታትሎ በመውሰድ በጠንካራ ልምድ እና ተሳትፎ ላይ ይገኛል፡፡ በሄነሪ ኳስፕርዧክ

የሚሰለጥነው የማሊ ብሄራዊ ቡድንን በአማካይ መስመር የሚጫወቱት አምበሉ ሰይዱ ኪዬታ እና ሞሃመድ ሲሶኮ እንዲሁም በአጥቂ መስመር የሚሰለፈውን ሞዲቦ ማይጋ መያዙና 4­-3-3 የአሰላለፍ ታክቲክ መከተሉ ወቅታዊ አቋሙን ያከብደዋል፡፡ 27 ተጨዋቾች ያሉበት የንስሮቹ ስብስብ 23 ከአገራቸው ውጭ የሚጫወቱ ፕሮፌሽናሎችን ያካትታል፡፡ በትራንስፈር ማርኬት ድረገፅ የወጣለት የተጨዋቾች ዝውውር ገበያ የዋጋ ግምቱ  24.5 ሚሊዮን ዩሮ ሲሆን አማካይ እድሜው 25.6 አመት ነው፡፡ የማሊ ብሄራዊ ቡድን ከፍተኛ ልምድ ባለው እና የቡድኑ ዋናው አምበል በሆነው ሰይዱ ኪዬታ ብቻ ከኢትዮጵያ የላቀ ነው፡፡  በስፔኑ ክለብ ባርሴሎና ከፍተኛ ዓለም አቀፍ እውቅና የተጎናፀፈው እና በርካታ ስኬቶች ያስመዘገበው የ34 ዓመቱ ሰይዱ ኪዬታ በፈረንሳይ ሊግ 1፤ በስፔን ላሊጋ፤ በቻይና ሊግና አሁን ደግሞ በጣሊያን ሴሪኤ ላለፉት 10 የውድድር ዘመናት

በመጫወት ከፍተኛ ልምድ ያካበተ  ነው፡፡ በመሃል አማካይ መስር የሚጫወተው ኪዬታ አሁን በጣሊያኑ ክለብ ሮማ ተዛውሮ እየተጫወተ ሲሆን በሳምንት 19ሺ ፓውንድ ይከፈለዋል፡፡ ነው፡፡ በትራንስፈር ማርኬት ድረገፅ በተገኘ መረጃ መሰረት ኪዬታ ከ5 አመት በፊት በዝውውር ገበያው የዋጋ ተመኑ 16 ሚሊዮን ዩሮ ነበረ፡፡ አሁን ግን ግምቱ ወደ 1 ሚሊዮን ዩሮ ወርዷል፡፡ ከ2000 እኤአ ጀምሮ በማላዊ ብሄራዊ ቡድን ሲጫወት 90

ጨዋታዎች አድርጎ 23 ጎሎች በስሙ አስመዝግቧል፡፡ በባርሴሎና ስኬታማ ቆይታ የነበረው ኪዬታ ሁለት

የሻምፒዮንስ ሊግ፤ እና የላሊጋ ዋንጫዎችን ጀምሮ 14 ዋንጫዎችን በመሰብሰብ ታሪክ የሰራ ነው፡፡

           የሞባይል ስልክ ተጠቃሚዎች ቁጥር በከፍተኛ ሁኔታ እያደገ በሚገኝባት ሰሜን ኮሪያ፣ በተጠቃሚዎች ላይ የሚታየውን የስነ-ምግባር ጉድለት ለመቅረፍ ሲባል አዲስ የአጠቃቀም መመሪያ መውጣቱን ቢቢሲ ዘገበ፡፡ ዮንሃፕ የተባለውን የሰሜን ኮሪያ የዜና ተቋም ጠቅሶ ዘገባው እንዳለው፣ በአገሪቱ የሞባይል ተጠቃሚዎች ላይ ከሚታዩ የስነ-ምግባር ጉድለቶች መካከል፣ ሰው በተሰበሰበባቸው አካባቢዎች ጮክ ብሎ ማውራትና መጨቃጨቅ ይገኙባቸዋል፡፡ አዲሱ የአገሪቱ የሞባይል አጠቃቀም የስነ-ምግባር መመሪያ እንደሚለው፣ ተጠቃሚዎች ህዝብ በተሰበሰበባቸው አካባቢዎች ድምጻቸውን ቀነስ አድርገው በትህትና መነጋገር ይኖርባቸዋል፡፡ በሞባይል ስልክ የሚደረጉ አላስፈላጊ ጭቅጭቆችን ለማስወገድ ሲባልም፣ የተደወለላቸው ሰዎች ጥሪያቸውን ሲመልሱ፣ ለደዋያቸው ማንነታቸውን ማስተዋወቅ ይጠበቅባቸዋል፡፡

የደዋያቸውን ማንነት እንዳወቁ መግለጽም ይገባቸዋል፡፡ ይህም ደዋዩ ራሱን ለማስተዋወቅ ጊዜ እንዳይፈጅ ያግዘዋል ተብሏል፡፡እ.ኤ.አ በ2008 የሞባይል ስልክ አገልግሎት ተጠቃሚ በሆነችው ሰሜን ኮሪያ፣ የአገልግሎቱ ተጠቃሚዎች ቁጥር ከ2 ሚሊዮን በላይ እንደደረሰ የጠቆመው ዘገባው፣ ይህም ሆኖ ግን አሁንም ድረስ አለማቀፍ ጥሪዎችን ማድረግ ክልክል ነው፡፡ የሞባይል ስልክ ባለቤት መሆን የሚችሉትም፣ በከፍተኛ የኑሮ ደረጃ ላይ የሚገኙ የማህበረሰብ ክፍሎች ብቻ ናቸው ብሏል፡፡ (ባለፈው ሳምንት ለንባብ ባበቃነው በዚህ ዜና ላይ፣ ‘ደቡብ ኮርያ’ ተብሎ የቀረበው በስህተት በመሆኑ ከይቅርታ ጋር ዜናውን አስተካክለን አቅርበናል)

       በአሜሪካ አማካይ የህይወት ዘመን እ.ኤ.አ ከ2012 ዓ.ም ጀምሮ ታይቶ የማይታወቅ ከፍተኛ መጨመር በማሳየት ወደ 78.8 ዓመት እንደደረሰ ኸልዝ ዴይ የአገሪቱ የፌደራል ባለስልጣናትን ጠቅሶ ሰሞኑን ዘገበ፡፡ የአሜሪካ የበሽታ ቁጥጥርና መከላከል ማዕከል ተመራማሪዎች እንደሚሉት፤ በአገሪቱ አማካይ የህይወት ዘመን ሊጨምር የቻለው ዜጎች ወደ ጤናማ የአኗኗር ዘይቤ በመመለሳቸው ነው፡፡ “አሜሪካውያን ረዥም ዕድሜ እየኖሩ ሲሆን፣ ዘላቂ በሽታዎችን አስቀድሞ ስለመከላከል የተሻለ ግንዛቤ ጨብጠዋል” ብለዋል፤ የጥናት ሪፖርቱ ዋና አዘጋጅ ዶ/ር ጂያኩዋን ዙ፡፡ “በህይወት የመቆያ አማካይ ዕድሜ የጨመረው ሰዎች ጤናማ ምግብ ስለሚመገቡና የአካል እንቅስቃሴ ስለሚሰሩ ነው” ብለዋል ዶክተሩ፡፡

እንዲያም ሆኖ ግን አሁንም ሴቶች ከወንዶች የበለጠ በህይወት የመቆየት አማካይ ዕድሜ እንዳላቸው ታውቋል፡፡ እ.ኤ.አ በ2012 ዓ.ም የተወለዱ የሴቶች በህይወት የመቆያ አማካይ እድሜ 81 ዓመት ሲሆን የወንዶች 76 እንደሆነ የሪፖርቱ አዘጋጅ ዶ/ር ዙ ተናግረዋል፡፡ በ2012 ዓ.ም ዕድሜያቸው 65 እና ከዚያ በላይ የነበሩ ሴቶች ተጨማሪ 20 ዓመት ገደማ ይኖራሉ ተብሎ የሚጠበቅ ሲሆን፣ ወንዶች ደግሞ 18 ዓመት ይኖራሉ ተብሏል፡፡ በሪፖርቱ መሰረት፤ ከ2011 እስከ 2012 ባለው ጊዜ በአሜሪካ የሞት መጠን ከ1 በመቶ በላይ መቀነስ አሳይቷል፡፡ ለሞት የሚዳርጉ ዋና መንስኤዎች በሚል የሚታወቁት ነገሮች አሁንም አልተለወጡም ተብሏል፡፡ በ2012 ዓ.ም 75 በመቶ ገደማ የሚሆነው ሞት የተከሰተው በልብ ህመም፣ በካንሰር፤ ዘላቂ በሆነ የታችኛው የመተንፈሻ አካላት በሽታዎች፣ በስትሮክ፣ በድንገተኛ ጉዳቶች፣ በመርሳት በሽታ፣ በስኳር፣ በኢንፍሉዌንዛና በሳንባ ምች፣ እንዲሁም በኩላሊት በሽታ እና ራስን በማጥፋት እንደነበር ሪፖርቱ ይጠቁማል፡፡ ከአስሩ ቀዳሚ የሞት መንስኤዎች በስምንቱ ላይ የሞት መጠን ከፍተኛ መቀነስ እንዳሳየ የሲዲሲ ሪፖርት ያመለክታል፡፡ በሌላ በኩል ምክንያቱ ባይታወቅም ራስን ማጥፋት በ2012 ዓ.ም ከቀደመው ዓመት በ2.4 በመቶ እንደጨመረ ዶ/ር ዙ ተናግረዋል፡፡

በኒውዮርክ ሲቲ ሌኖክስ ሂል ሆስፒታል ውስጥ የልብ ህመምን በመከላከል ላይ የሚሰሩት ዶ/ር ሱዛኔ ስቴይንባም፤ “ዋናዎቹ የሞት መንስኤዎች የአኗኗር ዘይቤን ተከትለው የሚመጡ ናቸው፡፡ በመከላከልና በህክምና ረገድ የተሻለ ሥራ እያከናወንን ነው” ብለዋል፡፡ የተሻለ ምግብ መመገብ፣ የአካል እንቅስቃሴ ማዘውተርና ሲጋራ ማጨስ ማቆም ጤንነትን ለመጠበቅ ወሳኝ እርምጃዎች እንደሆኑ የህክምና ባለሙያዎች ይናገራሉ፡፡በህይወት የመቆያ አማካይ እድሜ እንዲሻሻል ወይም እንዲጨምር የሚያደርገው ግን የተሻለ የህክምና ክብካቤ መኖር ነው ይላሉ - ዶ/ር ሱዛኔ፡፡ “በአብዛኞቹ የተለመዱት የሞት መንስኤዎች በአኗኗር ምርጫችን የተነሳ የሚከሰቱ ናቸው” የሚሉት የህክምና ባለሞያዋ፤ አመጋገባችንንም ሆነ የአካል እንቅስቃሴያችንን ከተቆጣጠርን ብዙዎቹን ዋነኛ የሞት መንስኤዎች መከላከል እንችላለን” በማለት ያስረዳሉ፡፡ “‹ህክምና - ተኮር› ከመሆን ይልቅ ‹መከላከል - ተኮር› ብንሆን የህይወት ዘመንን በእጅጉ ማርዘም ይቻላል” ብለዋል፤ ዶ/ር ሱዛኔ ስቴይንባም፡፡

         “እኛ አገር የመፃፍ ክህሎት ያላቸው በርካታ ናቸው፤ እየፃፉልን ያሉት ጥቂቶች ቢሆኑም፡፡
እነዚህ ጥቂቶችም የመፃፍ አቅማቸውን ያህል አልሰጡንም ፤ ወይ ሰንፈዋል - ወይ ያልተመቻቸው ነገር አለ፡፡ ፍቅረ ማርቆስ ደስታ፣ በዕውቀቱ ስዩም፣ አለማየሁ ገላጋይ፣ እንዳለጌታ ከበደ፣ ሰርቅ ዳ.፣ ሌሊሳ ግርማና መሰሎች ባላቸው ልክ /በዕድሜያቸው ልክ እንደማለት/ ብዙ ለማሳተምና ያላቸውን ለመስጠት የሚታትሩ ተጠቃሾች ናቸው፡፡ በእርግጥ ካላቸው ተሰጥኦና አቅም አንጻር ያሳተሟቸው ሥራዎች ማነሳቸው የሚከነክኑን እንዳሉበትም ልብ ይሏል፡፡ አዳምን ግን በተለየ ዓይን እንየው፤ በብቃትና በጥራት ያለውን ያለስስት እየሰጠን ነው፡፡
 /በዓሉና አዳም ከሚመሳሰሉባቸው ነገሮች አንዱ፣በተከታታይ በጥራት መፃፋቸውና ያንንም ለህዝብ ማድረሳቸው

ነው፤ ከአስር ዓመት ባልበለጠ ጊዜ ውስጥ ሁለቱም ከሰባት በላይ መጻህፍት ፅፈዋል፡፡/
አዳም ወደ ራሱ አብዝቶ የሚመለከት በመሆኑ ሰቅዞ ይይዛል፡፡
ለእኔ አዕምሮ የሚያክ ደራሲ ነው፤ የትዝታ ዘመኑን /ረጅም ጊዜ ውጭ ነውና እየኖረ ያለው/ በጥፍሩ ሲቧጥጥ፣

እኛም ባልኖርንበት ዘመን ትዝታችንንና ኑሮአችንን እንድንቧጥጥ ዕድል ይሰጠናል - አገናኝ ድልድይ በመሆን፡፡ አሰላሳይ ደራሲ ስለሆነ  የቃላት ጨዋታው ሁሉ ልቡና ላይ ነው - እያነበብከው አብረኸው ታሰላስላለህ፤ ኑሮህን፣ ዘመንህን፣ አገርህን!!
አዳም <<post modernism>> አፃፃፍ የገባው ነው፡፡
ከታሪክ አወቃቀርና ከመቼት ብሎም ከሴራ በላይ በድርሰቱ ይዞት የሚመጣው ቅርፅ የሚያሳስበውና ለእሱም

አብዝቶ የሚሳሳ ይመስላል፡፡ ቅርፅና አዳም ጋብቻ ፈፅመዋል - እንደሱ ገለፃ ‹‹የእንጀራ ቅርፅን›› አስተዋውቆናል፡፡ ይህ የራሱን መንገድ ይዞ የሚፈስ ቦይ ነው እንድንል ያስችለናል፡፡ በዚያ ወንዝ ውስጥ በተለይም ከ“ግራጫ

ቃጭሎች” እስከ አሁኑ “መረቅ” ድረስ ባለው ቅርፁ እከሌን  ይመስላል ለማለት ፊት አይሰጥም - አዳም በቃ አዳምን ይመስላል፡፡
 አዳም በሰው ኮቴ ላለመራመድ ያደረገው ፣ ከ“ግራጫ ቃጭሎች” በኋላ ተሳክቶለታል - በእኔ እምነት፡፡ አዳም የሰው ዳና አላዳመጠም፣ አዳም በራሱ መንገድና በራሱ ፋና ነው የነጎደው፤ በቋንቋና በሃሳብም ቢሆን ልቀቱ

ከፍታውን ይመስክሩለታል”
          - ደመቀ ከበደ  (ገጣሚ)


“የሥነፅሁፍን ሥራ ከማንም በላይ የሚፈትሸውና  የሚያቆየው ጊዜ ባለሟሉ ነው።  የአዳም መጻህፍት  ከጊዜ ጋር ለወደፊትም በአገራችን የሥነፅሁፍ ታሪክና አፃፃፍ ዘይቤ፣ የራሳቸው  ትልቅ ድርሻና ቦታ ይኖራቸዋል።አዳም «ህጽናዊነት» የሚል ስያሜ የሰጠው የራሱ የሆነ የአፃፃፍ ዘይቤ መፍጠር የቻለ ደራሲ ነው።  ይህም ጥቃቅንንም ሆኑ ግዙፍ ነገሮችን፣ ሰዎችን (ገፀ ባህሪያት)፣ ስሜቶችን፣ ሁኔታዎችን በማያያዝና በማዛመድ አንባቢዎች አእምሮ ውስጥ ትውስታና ትዝታም የሚጭር የአፃፃፍ ዘይቤ ነው። በታሪክ ይዘታቸው በጣም መሳጭና ወደ ራሳችን ውስጥ አስገብተን፣ እራሳችንን እንድንፈትሽና እንድንጠይቅ የሚያደርጉ ናቸው።   አንዳንድ  የሴት ገፀ ባህርያቱ፣ የሴቶችን አስተሳሰብና  ባህሪያት በግልፅ (ሳይሸፋፍንና ሳያድበሰበስ)

የሚያሳዩ ናቸው።  ሴት ልጅ በወጣትነት እድሜዋ የሚያጋጥማትን  ስነልቦናዊ ፈተናዎችና ከባሕላችን ጋር ለመራመድ (ለመሄድ) የምታደርገውን ነገሮች--- አስመሳይነትን በግልፅ የምናይባቸው ገፀ ባህሪያት አሉ። ለምሳሌ “እቴሜቴ የሎሚ ሽታ” ውስጥ “ (ሽልንጓ) የመጨረሻዋ የቀበሌ 01 ድንግል” ውስጥ ያለችው የነፃነት ገፀ ባህሪ፣ የሴት ልጅን  ሥነልቦናዊ  ፈተና  በደንብ ያሳየናል። በእኛ ሕብረተሰብ ውስጥ ሴት ልጅ “ጨዋና ጭምት” መሆን አለባት ተብሎ ይጠበቃል። “ጨዋ” ማለት ምን ማለት ነው? ይህን እንድንጠይቅና እንድንፈትሽ የሚያደርጉ ገፀ ባህሪዎች ናቸው። በ“ይወስዳል መንገድ ያመጣል መንገድ” ውስጥ ያሉት እትዬ ወርቄ  ደግሞ አገር ወዳድነትን፣ እናትነትን፣ እማማ ኢትዮጵያን ራሷን የሚስልበት ገፀ ባህሪ ናቸው። ለዚህም ነው ጊዜና ዘመን የማይሽራቸው መፅሐፍት የሚመስሉኝ።
እነሆ አሁን ደግሞ 600 ገጾች ያሉት  ዳጎስ ያለ አዲስ ልብወለድ፣ «መረቅ» በሚል ርዕስ ለአንባቢያን አቅርቧል።”
ሮማን ተወልደ ብርሃን ገ/ እግዚያብሄር (አድናቂ፣ ከለንደን)



አዳም ስለራሱ….
 “ስጽፍ አልለፋም!...”
 “አጣርቼ የማስወጣበት ወንፊት የለኝም!”
 (‘በስራዎችህ ከጥቃቅን ዝርዝሮች፣ የማይደፈሩ እስከሚመስሉ ነገሮች ደፍረህ ታወጣለህ፣ የገጸ ባህሪያቱን ውስጣዊ ስሜት፣ የማህበረሰቡን ህጸጾች ጨክነህ ታፍረጠርጣለህ…’ ተብሎ ሲጠየቅ፣የሰጠው ምላሽ)“ነገሮችን ማየት እወዳለሁ እንጂ አልንቀለቀልም፡፡ ጥቃቅን የሚመስሉ ነገሮችን አልንቃቸውም፡፡ አያቸዋለሁ፡፡

እረፍት ሳገኝ ደግሞ፣ ተመልሼ በደንብ አያቸዋለሁ… የሚጻፉ መስለው ከታዩኝ፣ እጽፋቸዋለሁ!...”
 “When I want to write, I write!”
 (‘ለመጻፍ የሚያነሳሳህ ምን አይነት ሁኔታ ነው?’ ለሚል ጥያቄ የመለሰው)
“ ‘ፍቅር እስከ መቃብር’ ውስጥ ያለችው ሰብለ ወንጌል፣ እንደ መልዓክ ናት - ከሰው ይልቅ ለመልዓክት የቀረበ

ባህሪ የተላበሰች፡፡ እኔ የሞከርኩት፣ ሰብለን ‘ሰው’ ሆና እንድትታይ ለማድረግ ነው!...”
.“Mezgebu is just living. He knows nothing about precision and the like.”
(ባለፈው ሳምንት ቅዳሜ ደራሲ አዳም ረታ፣ ከአድናቂዎቹ ጋር በተገናኘበት የቡና ስነስርዓት ላይ ከተናገረው የተወሰደ)

          የመውለድ አቅምን ይቀንሳል ተብሏል የአልኮል መጠጥ የሚወስዱ ወንዶች የዘር ፍሬያቸው በመጠንና በጥራት እንደሚቀንስና በመውለድ አቅማቸው ላይ ተፅዕኖ እንደሚፈጥር በስታንፎርድ ዩኒቨርሲቲ የተሰራ ጥናት አመለከተ፡፡ “ብዙ ጥናቶች የአልኮል መጠጥ ከመጠን በላይ መውሰድ በአጠቃላይ ለጤና እንደማይበጅ አረጋግጠዋል፡፡ አልኮል በመጠኑ መውሰድ በሥነተዋልዶ ጤና ላይ አሉታዊ ተፅዕኖ እንዳለው የሚያሳይ ጥናት እምብዛም የለም” ይላሉ በስታንፎርድ ዩኒቨርሲቲ የህክምና ት/ቤት ረዳት ፕሮፌሰር የሆኑት ዶ/ር ማይክል ኢሰንበርግ፡፡ በሳምንት 40 ብርጭቆ ወይም ከዚያ በላይ የአልኮል መጠጥ የሚወስዱ ወንዶች የዘር ፍሬያቸው እጅግ በጣም እንደሚቀንስ ጥናቱ ቢያረጋግጥም፤ ጥናት አድራጊዎቹን ያስገረማቸው ሌላም ነገር አለ፡፡ በሳምንት አምስት ብርጭቆ የአልኮል መጠጥ (ቢራ ወይም የወይን ጠጅ ሊሆን ይችላል) ብቻ የሚጠጡ ወንዶች ላይም ተመሳሳይ ችግር እንደተስተዋለ በሳውዘርን ዴንማርክ ዩኒቨርሲቲ ፕሮፌሰርና የጥናቱ ዋና ተመራማሪ ዶ/ር ቲና ኮልድ ጄንሰን ተናግረዋል፡፡

በጥናቱ አካሄድ የተነሳ በወንዶቹ የዘር ፍሬ ላይ የታየው ለውጥ በአልኮል መጠጡ ሳቢያ የመጣ ይሁን አይሁን ለማወቅ አልተቻለም ይላሉ - አጥኚዎቹ፡፡ “ለዘር ፍሬው በቁጥርም ሆነ በጥራት መቀነስ እንደ ምግብ፣ ሲጋራ፣ የሰውነት ክብደት ወዘተ… ያሉ ሌሎች ነገሮች ጋር ለማያያዝ ብንሞክርም ግንኙነት እንዳላቸው የሚያሳይ ነገር አላገኘንም፡፡ ችግሩ ከአልኮል መጠጣት ጋር በተያያዙ ሌሎች ጉዳዮች ሊከሰት ይችላል የሚለውን ግን ውድቅ አላደረግነውም” ብለዋል ጄንሰን፡፡ ጥናቱ ለውትድርና አገልግሎት ብቁ መሆን አለመሆናቸውን ለማረጋገጥ የጤና ምርመራ ያደረጉ ከ1 ሺ 200 በላይ የዴንማርክ ወጣት ወንዶችን ያካተተ ሲሆን ዕድሜያቸው ከ18 እስከ 28 የሚደርስ ነው፡፡ የአልኮል መጠጥ ልማዳቸውን የተመለከተ መጠይቅ እንዲሞሉ ከመደረጋቸውም በተጨማሪ የዘር ፈሳሽ ናሙናና ደም ሰጥተዋል፡፡

ከምርመራው በተገኘው ውጤትም በየሳምንቱ አንድ ብርጭቆ አልኮል ከሚጎነጩት ይልቅ በየሳምንቱ አምስት ብርጭቆ የአልኮል መጠጥ የሚወስዱት የዘር ፍሬያቸው በመጠንም፣ በጥራትም፣ በጤነኝነትም እጅግ ዝቅ ያለ መሆኑ ተረጋግጧል፡፡ በሳምንት ቢያንስ 25 ብርጭቆ አልኮል የሚጨልጡ ወንዶች፤ የዘር ፍሬያቸው በመጠንም ሆነ በጥራት በእጅጉ ያሽቆለቆለ መሆኑን ለማወቅ ተችሏል፡፡ በሳምንት 40 ወይም ከዚያ በላይ በሚጠጡ ወንዶች ላይ በተካሄደው ጥናት፤ በሳምንት እስከ 5 ብርጭቆ ድረስ ከሚጠጡት በ33 በመቶ ያነሰ የዘር ፍሬ ይዘት እንደነበራቸው ታውቋል፡፡ “ብዙ ወንዶች ዝምተኛ ጠጪዎች ናቸው፤ ይሄ ባህርያቸው እንደሚጎዳቸው ግን አይገነዘቡም፡፡ ዝምተኝነታቸው ከሚፈልጉት በላይ እንዲጠጡ ያደርጋቸዋል” ያሉት ደግሞ በሂዩስተን በሚገኝ ሆስፒታል የማህጸንና የወሊድ ህክምና ባለሙያ የሆኑት ዶ/ር ማይክል ኸርድ ናቸው፡፡ እሳቸው እንደሚሉት፤ ስካር ሆርሞኖችንና በሰውነታችን ውስጥ የሚገኙ ሌሎች ኬሚካሎችን (ኮርቲሶል፣ ግሉኮስ፣ ኢንሱሊንና የወንድ ሆርሞን) እንዲለወጡ ያደርጋቸዋል፡፡ “እኒህ ሁሉ የዘር ፍሬ ጥራት ላይ ችግር ያስከትላሉ፤ ጥራቱ ዝቅ ያለ የዘር ፍሬ ደግሞ ፅንስ የማፍራት ሂደቱን ሊያስተጓጉለው ይችላል” ብለዋል ኸርድ፡፡

Saturday, 11 October 2014 13:25

የቀጨኔ ልጆች ምን ይላሉ?

       ዛሬም “ቡዳ በልቶት ነው” ከማለት አልተላቀቅንም!

            ከፒያሳ በ2.8 ኪሎ ሜትር ርቀት ላይ የሚገኘው ቀጨኔ፤ በአዲስ አበባ ከተማ ከሚገኙ ሰፈሮች ውስጥ አንዱ ነው፡፡ ከሰሜን ሸዋ ተነስተው በአካባቢው የሰፈሩት የቀጨኔ ነዋሪዎች ከእስራኤል እንደመጡ ይነገራል፡፡ የአካባቢው ሰዎች በእጅ ሙያ በተለይ በሸክላ ስራና በሽመና የተሰማሩ በመሆናቸው “ቡዳ” በሚል አሉታዊ ተፅዕኖ የሚያሳድር ስያሜ የሚጠሩ ሲሆን “የቀጨኔ ሰዎች ሌሊት ወደ ጅብ በመቀየር ሰው ይበላሉ” የሚለው አመለካከትም ሙሉ በሙሉ አለመቀየሩን የሰፈሩ ነዋሪዎች በቅሬታ ይገልፃሉ፡፡ የህብረተሰቡ አመለካከት ከቀድሞው እየተሻሻለ መምጣቱን ባይክዱም ችግሮቹ ግን አሁንም እንዳሉ ነው ነዋሪዎች የሚናገሩት፡፡

በቀጨኔ ተወልዶ ያደገው ሰለሞን አስፋው እንደሚለው፤ የአካባቢው ሰዎች በሚደርስባቸው ጫና የተነሳ አብዛኛውን ጊዜ ሰፈራቸው ቀጨኔ እንደሆነ አይናገሩም፡፡ ሲጠየቁ ወይም መናገር የግድ ከሆነባቸው ሾላ ወይም አዲሱ ገበያ ገባ ብሎ በማለት ነው የሚመልሱት፡፡ ሰፈሬ ቀጨኔ ነው ብሎ መናገር ለብዙ ሰው “እኔ ቡዳ ነኝ” እንደማለት ነው የሚቆጠረው፡፡ አንዳንድ ጊዜ ታክሲ ውስጥ ስለቀጨኔ ሲወሩ የምሰማቸው ነገሮች በጣም ይገርሙኛል፤ ሁሉም የሚያወሩት ራሳቸው በቀጥታ ያጋጠማቸውን ሳይሆን አንዱ ሰው ከሌላ ሰው ሰምቶ የነገራቸውን ነው፡፡ “ሰው በቡዳ ተበልቶ” የሚለው ወሬ መቆሚያ የለውም፡፡ ሁልጊዜ ይወራል፡፡ መቼም ሰው እንደዚህ “በቡዳ እየተበላና እየሞተ” የሟች ቤተሰቦች የሆነ ነገር ማለታቸው አይቀርም ነበር፡፡ ነገሩ ወንጀል ስለሆነም ይፋ ይሆን ነበር ይላል ሰለሞን፡፡

አንድን ህዝብ “ሰው ትበላለህ” ብሎ መናገር ራሱ ትልቅ ወንጀል ነው፡፡ በየቦታው የምትሰሚው ነገር ላይ ክርክር ብታነሺ ውሉ ያልተገኘለት ክር እንደመምዘዝ ስለሚሆን ዝም እላለሁ፡፡ የሚያድጉ ትንንሽ ልጆች በማንነታቸው እንዳያፍሩና ለተፅዕኖ እንዳይበገሩ ግን የተቻለንን ሁሉ እንሰራለን፡፡ አንዳንድ ጊዜ ሰዎች “ከቀጨኔ” ብለው ሬዲዮ ላይ ጥያቄ ሲመልሱ ወይም ዘፈን ሲመርጡ በጣም ደስ ይለኛል፤ ምክንያቱም ሰፈሩን መጥራት እየተለመደ እንዲመጣ ያደርገዋል፡፡ ሲል አስተያየቱን ሰጥቷል፡፡ ሰለሞንን ጨምሮ ያነጋገርኳቸው ዳዊት ጥላሁንና ሰላማዊት ወንድምአገኘሁ የመጀመሪያ ደረጃ ትምህርታቸውን እዚያው ሰፈራቸው በሚገኘው “ቀጨኔ ደብረሰላም” ትምህርት ቤት በመማራቸው የተለየ ነገር ሳያዩ ነበር ያደጉት፡፡ ፈተናዎችን መጋፈጥ የጀመሩት ወደ ሁለተኛ ደረጃ አልፈው ሌላ ትምህርት ቤት ሲመደቡ ነው፡፡ ሰላማዊት የሁለተኛ ደረጃ ትምህርት ቤት ገጠመኟን እንዲህ ታወጋለች፡- “ኤለመንተሪ የራሳችን ማህበረሰብ የሰራው ትምህርት ቤት ውስጥ ስለተማርን ጓደኝነታችን ከማህበረሰባችን ሰው ጋ ነበር፡፡ እኔ ለሁለተኛ ደረጃ ትምህርት ቤት መነን ነበር የተመደብኩት፡፡ ክፍል ውስጥ ከአንድ የሰፈሬ ልጅና ከሌላ ሰፈር ልጅ ጋር ነበር የምንቀመጠው፡፡

ከልጅቷ ጋር በጣም ጥሩ ቅርበት ነበረን፡፡ የቀጨኔ ልጆች መሆናችንን ስታውቅ ግን ወዲያው ተቀየረች፣ ከኛ ጋር ምግብ መብላት አቆመች፣ ለሌሎችም ነግራ ሁሉም እንዲያገሉን አደረገች፡፡ እንዲያም ሆኖ እኔ ሰፈሬን ደብቄ አላውቅም፤ መናገር ባለብኝ ቦታ ሁሉ የቀጨኔ ልጅ እንደሆንኩ እናገራለሁ፡፡ ነገር ግን ሌላው ሰው ስለኛ ማህበረሰብ የሚያወራውን ነገር ስትሰሚ በውስጥሽ ጥያቄ ይፈጠራል ትላለች፡፡ የሆነ ጊዜ ላይ እናትና አባቴ ጅብ ሆነው ሲቀየሩ ለማየት ቁጭ ብዬ አድር ነበር፡፡ እኔ ወደ ጅብ የምቀየረው ሳድግ ነው እንዴ ብዬ ራሴንም እጠይቅ ነበር፡፡ እናትና አባቴ ግን ሌሊት ተነስተው ቤተክርስቲያን ሲሄዱ ነበር የማየው፡፡” አንድ ጊዜ አንድ ሰው ማታ ሰክሮና ተፈነካክቶ ጉድጓድ ውስጥ እግሮቹን ጅብ ለኮፍ ለኮፍ አድርጓቸው፣ ጠዋት ላይ በህይወት ይገኝና ሀኪም ቤት ይወሰዳል፡፡ የሀኪም ቤቱ ሰራተኞች “የት ነው የተገኘው?” ብለው ይጠይቃሉ፡፡ ቀጨኔ ጉድጓድ ውስጥ መሆኑ ሲነገራቸው፤ “አይ እዚያማ ሰዎቹ ራሳቸው ጅቦች ናቸው፤ ራሳቸው በልተውት ነው” አሉ ይባላል፡፡ የሚወራው ነገር የሚፈጥረው ጫና እጅግ ከባድ ነው፡፡ ለምሳሌ እኔ የሽመና ሙያ አውቃለሁ፤ ከዚያ አልፎም ዲዛይነር ነኝ፡፡ የሆነ ወቅት ላይ “ዲዛይነር” ብዬ ራሴን ማስተዋወቅ ስጀምር፣ የተወሰኑ ሰዎች ግርግር ፈጥረውብኝ ነበር፡፡ ምክንያቱም እዚያው ጉድጓድ ውስጥ ሆኜ ሽመናውን እንድሰራ እንጂ እንዳድግ አይፈለግም፡፡

ይህን ግርግር የፈጠሩት ሰዎች ደግሞ ሙያውን በትክክል ጠንቅቆ የሚያውቀው ሰው የሰራውን ስራ በማይረባ ዋጋ ገዝተው፣ ደህና ስምና ሱቅ ስላላቸው በውድ ዋጋ የሚሸጡ ናቸው፡፡ በጣም የሚገርመኝ እኛ ሰፈር ጅብ ሞቶ ቢገኝ ሰዎች መጥተው አይኑን፣ ቅንድቡን፣ ጆሮውን… ቆራርጠው ይወስዳሉ፤ ምን ይሰራላችኋል ስትያቸው፤ “የቡዳ መድሃኒት ነው” ይሉሻል፡፡ ሰዎች ወደኛ ሰፈር ሲመጡ እንደ ነጭ ሽንኩርት አይነት ለቡዳ መከላከያ ነው ብለው የሚያምኑበትን ነገር ደብቀው ይይዛሉ፡፡ በሚወራው ወሬ ምክንያትም የቤት ኪራይ ርካሽ ስለሆነ፣ የኛ ማህበረሰብ ያልሆኑ ተከራዮች፤ ልጆቻቸው አንገት ላይ የቡዳ መከላከያ የሚሉትን ነገር ያስራሉ፡፡ የኛን ሸማ ለብሰው፣ በኛ ሸክላ አብስለው በልተው፣ የሚያወሩት ነገር ምን እንደሆነ ሳስበው ግራ ይገባኛል ብላለች - ሰላማዊት፡፡ የከፍተኛ ትምህርቱን ለመማር አዲሱ ገበያ ተመድቦ እንደነበር የሚናገረው ዳዊት፤ ከተለያዩ የከተማዋ ክፍሎች በሚመጡ ተማሪዎች የሚወራው ወሬ የተሳሳተ ስለነበር ከቀጨኔ ነው የመጣሁት አልልም ነበር ብሏል፡፡ “ሰው ወደ እኛ ሰፈር እንደሚመጣ ሲታወቅ እንዳትሄድ ወይም ተጠንቀቅ ይባላል፡፡

በቅርብ ጊዜ የክፍለሀገር ልጅ የሆነች የጓደኛዬ ባለቤት እኛ ጋ መምጣት ፈልጋ፣ ወንድሟ ‹እዚያ ሰፈር ከሄድሽ አበቃልሽ፤ በህይወት አትመለሽም› ብሏት እንደነበር አጫውታናለች፤ ቤታችን አድራ ስትሄድም በሚወራው ነገር ግራ እንደተጋባች ነግራን ነበር ብሏል፡፡ አብዛኛው የቀጨኔ ነዋሪ የተሰማራበትን የእጅ ሙያ ሥራ በተመለከተ ሦስቱም ወጣቶች በሰጡኝ አስተያየት፤ የቀጨኔ ሰዎች የራሳቸውን ምርቶች አደባባይ አውጥተው ለመሸጥ ያለባቸው ጫና ከፍተኛ በመሆኑ የስራቸው ውጤት ተጠቃሚ አይደሉም፡፡ የሥራው ተጠቃሚዎች ለሸማ ስራ ከዋሉት ነገሮች አንዳቸውንም እንኳ የማያውቁ ሌሎች ሰዎች ናቸው፡፡ የቀጨኔ ሰው እዚያው ሰፈሩ አፈር ላይ ሆኖ የሰራውንና በተለያዩ ጫናዎች ምክንያት ራሱ ይዞት የማይወጣውን ምርት ተቀብለው፣ በከተማዋ ባሉ ሱቆች መሸጥ የሚችሉ ናቸው እየተጠቀሙ ያሉት፡፡ ማህበረሰቡ ተፅዕኖውን ሰብሮ ለመውጣት አልቻለም፡፡ በታሪኩም ከቦታ ቦታ ሲሳደድ የመጣ በመሆኑ፣ ፍራቻው እስካሁን ከውስጡ አልወጣም፤ ብለዋል፡፡ በቅርቡ በህብረት ስራ ተደራጅተው እንዲሰሩ በመንግስት ተወስኗል፡፡ በዚህ አጋጣሚ “ራስ አገዝ የሴቶች ድርጅት” ሴቶችን ቀጨኔ እያመጡ የሸክላ አሰራር እንዲሰለጥኑ በማድረጋቸው ምስጋና ይገባቸዋል ይላሉ - ወጣቶቹ፡፡ ዳዊት እንደሚለው፤ “ቡዳ” የሚለው ቃል በጊዜ ሂደት ትርጉሙን እየለወጠ መጣ እንጂ አዋቂ ጠቢብ ማለት ነበር፡፡ በነገራችን ላይ የመጀመሪያው ሸክለኛ፣ የሰውን ልጅ በጭቃ የሰራው እግዚአብሔር ነው፤ እሱንስ ምን ሊሉት ይሆን? ዳዊትና ጓደኞቹ ይጠይቃሉ፡፡

(አንጋቻ ፉር ይጠብጥቲ ቤቶ ጦት ኤያተኩሺ)
ከዕለታት አንድ ቀን አንድን ዲታ የገጠር ሰው አውቶብስ መናኸሪያ አካባቢ ሌቦች አይተው ገንዘቡን ከኪሱ

ሊወስዱ ያንዣብቡበታል፡፡ ሰውዬው በጣም ደክሞታል፡፡ በአቅራቢያው ወደሚገኝ ቤተክርስቲያን ሄዶ ጥቂት

አረፍ ማለት ይሻና ወደዚያው ቤተክርስቲያን ሄዶ ጥቂት አረፍ ማለት ይሻና ወደዚያው ያመራል፡፡
ሌቦቹም ባገኙት አጋጣሚ ብሩን ሊመነትፉት “እንከተለው፣ እንከተለው” ተባብለው ማንዣበባቸውን ይቀጥላሉ፡፡
ሌቦቹ ሰውዬውን ከግራ ከቀኝ ከበው ሲከተሉት ፖሊስ ጠርጥሮ እነሱን እየተከተላቸው ኖሯል፡፡
ሰውዬው ቤተክርስቲያን ገባ፡፡
ሌቦቹም ተከትለውት ገቡ፡፡
ሰውዬው ሳር ላይ ጋደም አለ፡፡ ሌቦቹም ዙሪያውን ተጋደሙ፡፡
አፍታም ሳይቆይ ሰውዬው እንቅልፍ ድብን አድርጎ ወሰደው፡፡
ሌቦቹ በጣም ቀርበው ደረት ኪሱ ያለውን ገንዘብ ለማውጣት ሲሞክሩ ፖሊሶቹ ወደሌቦቹ መጡ፡፡
ከሌቦቹ አንደኛው ፖሊሶች እንደደረሱባቸው በመገንዘብ፣ ከኪሱ ምላጭ አውጥቶ ሰውዬውን መላጨት ጀመረ፡፡
አንደኛው ፖሊስ - “ምንድነው? ምን እያደረጋችሁ ነው?” ሲል ጠየቀ፡፡
አንደኛው ሌባ - “አይ ጓደኛችን ነው፡፡ ደክሞት ጋደም ብሎ ነው፡፡ ፀጉሩ በጣም ስላደገ ላጩኝ ብሎን ነው፡፡

ድንገት እንቅልፍ ወሰደው፡፡”
ፖሊሱም፤
“ደህና፡፡ ቀጥሉ” ብሎ ሄደ፡፡
ሌቦቹ፤
“ስለጥንቃቄህ እናመሰግናለን” አሉት፡፡
ሌቦቹም ከራሱ ላይ ፀጉሩን፣ ከደረት ኪሱ ብሩን፣ ላጭተው ሲያበቁ ተነስተው ይሄዳሉ፡፡
ሰውዬው ከሰዓታት በኋላ ከእንቅልፉ ይነቃል፡፡
የሰላም እንቅልፍ በመተኛቱ፤
“ተመስገን” እያለ ደረቱ ላይ ሲያማትብ፤ ደረት ኪሱ ቅልል አለበት፡፡ እጁን ኪሱ ከቶ ቢያይ ብሩ የለም፡፡
“ወይኔ ብሬ! ብሬን ዘረፉኝ!” እያለ በሁለት እጁ ጭንቅላቱን ይዞ ሊጮህ ሲሞክር የራስ ፀጉሩ የለም፡፡
ይሄኔ ጥቂት አሰብ አድርጎ ፀጉር - አልባ መሆኑን በደንብ ሲገነዘብ፤
“እፎይ! ለካ እኔ አይደለሁም!” ብሎ ተፅናንቶ መንገዱን ቀጠለ፡፡
                                     *       *          *
በቁም ከሚላጩ ሌቦች ይሰውረን!
መቼም ቢሆን መች ማንነታችንን ከሚያስዘነጋ አደጋ ይጠብቀን፡፡ ህልውናችንን ጥያቄ ውስጥ ከሚያስገባ ሁኔታ ያድነን፡፡ የቱንም ያህል ብናንቀላፋ፣ የቱንም ያህል ቸልተኛ ብንሆን፣ የቱንም ያህል ግብዝ ብንሆን፤ “እፎይ! እኔ አይደለሁም!” ከማለት ያውጣን፡፡
በሀገራችን ከተከሰቱ ችግሮች አንዱ “እኔን እስከደገፈ ድረስ አምነዋለሁ” የማለት አባዜ ነው፡፡ ሌብነቱን ያበዛው፣ እምነቱን ያቀጨጨው፣ በቀላሉ ማታለልን ያበረታታው፤ “ከታላላቅ ባለሥልጣናት ጋር የዋለ አጭበርባሪ ሊሆን አይችልም” ብሎ ማለትን እጅግ ያጎለበተው ሰውን የማመን ባህል ነው፡፡ ማመናችንን እንመርምር! ሀገራችን ችግር በገጠማት ቁጥር ከመራወጥና ይይዙት ይጨብጡትን ከማጣት፣ ተገዶም ከመንገድ ከመውጣት አስቀድሞ “ያቀድነው ባይሳካስ፣ ያልጠበቅነው ነገር ቢከሰትስ?” ብሎ ራስን መጠየቅ ትልቅነት ነው፡፡ ማናቸውም ችግር ራስን ለማዘጋጀት ይጠቅማልና ያቀድኩትን በችኮላ እፈፅማለሁ ብሎ መሯሯጥም “ሲሮጡ የታጠቁት ሲሮጡ ይፈታል መሆኑን ቀድሞ ማውጠንጠን ነው፡፡
ባልታዛር ግሬሺያን የተባለ ፈላስፋ፤ እንዲህ ይለናል፡-
“ታላላቅ ችሎታ ያላቸው ሰዎች ቸኩለው እርምጃ ከመውሰድ ይቆጠባሉ፡፡ ምነው መውጣት አንድ ጉዳይ ውስጥ ቸኩሎ እጅን ካስገቡ በኋላ፤ ያ ከመግባት ይልቅ የከበደ ነውና፡፡ አንዳች አዲስ ነገር ሲከሰት ፍርድህን ይፈታተንሃል፡፡ በአሸናፊነት መውጣት ከሚጠይቅህ አቅም ይልቅ፤ ቸኩሎ ከመወሰን መቆጠብ ትንሽ ጉልበት ነው የሚጠይቀው፡፡ አንድ ኃላፊነትና ግዴታ ሌላ ኃላፊነትና ግዴታን እንደሚወልድ አትርሳ፡፡ ያ እየተጫነህ ስትመጣ ወደ መንኮታኮት እጅግ ተቃረብክ ማለት ነው፡፡”ይሄ ለእኛ ትልቅ ተሞክሮ ሊሆነን ይገባል፡፡ በሩቅ ከለየላቸው ጠላቶች ይልቅ በውስጣችን ያሉትን መጠንቀቅም አንዱ መርሀችን ሊሆን ይገባል፡- “ለሰለሰ ብለህ እባብ ትታጠቃለህ ወይ?” የሚለው የትግሪኛ ተረት ይሄንን ጠቅልሎ ያስቀምጥልናል፡፡
በሀገራችን፣ የፖሊተካ፣ የኢኮኖሚና ማህበራዊ ንፍቀ-ክበብ ውስጥ ብርቱ ቦታ ሊሰጠው የሚገባ ነገር አደብ መግዛትና ሆደ-ሰፊ መሆን ነው፡፡ በቀላሉና በትንሹ ነገር ሁሉ ቱግ ማለት፣ ሲያሸንፉ ከልኩ በላይ ዘራፍ ማለት፣ ሲሸነፉ መድረሻ ማጣትና ዓለም ጨለመች ማለት፤ ለክፉ ይዳርጋል፡፡ “ላናድህ ያለ እሳት ሲጭር እሳት ፍለጋ አትሂድ፡፡ ማገዶውን አርጥብ” እንዲል መፅሐፈ - ተረት፤ በብስለት እንጂ በጉልበት ለውጥ እንደማናመጣ ልብ እንበል፡፡ ዛሬ ላደርገው ያሰብኩትን ነገር በቀጣዩ ዓመት ባደርገውስ? ብሎ ቆም ብሎ ማሰብ “የቸኮለች አፍሳ ለቀመች” ከመባል ያድነናል፡፡ ብዙ በችኮላ የተከናወኑ እንቅስቃሴዎች ሽባ አድርገው ሊያስቀሩን እንደሚችሉ ያስወረዱ አብዮቶች (abortive revolutions) ታሪክ ይነግረናል፡፡ ለማናቸውም፤ ግዴታችን የሆኑትን ነገሮች ለይተን እንደግዴታነታቸው መቀበል፣ ኃላፊነት የሚጠይቁትን ጉዳዮች እንደኃላፊነት አጥብቆ ይዞ መወጣት፣ አሌ የማይባልና ተጠያቂነትን የተሸከመ ተግባር ነው፡፡ ለሀገር ዕድገትና ለህዝብ ጥቅም ሲባል፤ መሪና ተመሪ፣ ገዢና ተገዢ፣ አለቃና ምንዝር፣ ሥልጣን ላይ ያለፓርቲና ተቃዋሚ … ሹመኛና ሿሚ፤… ሁሉም ሁነኛ ኃላፊነትና ግዴታውን ጠንቅቆ ማወቅ አለበት፡፡ ምነው ቢሉ፤ “ድመት አይጥ እነዲይዝ ተብሎ ችቦ አይበራለትምና!” 

               በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን የመንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ቤተ ክህነት ጽ/ቤት ዋና ሥራ አስኪያጅ፤ በፓትርያርኩ ልዩ ጽ/ቤት ተጠርቶ የተካሔደው ስብሰባ የጠቅላይ ቤተ ክህነቱን ወቅታዊ ኹኔታ የማይገልጽ፣ መዋቅሩን ያልጠበቀ እና ጽ/ቤታቸው የማያውቀው መኾኑን በመግለጽ ተቃወሙ፡፡ ‹‹የቤተ ክርስቲያንን አስተዳደራዊ አስተሳሰብ ማበልጸግ›› በሚል ርእስ ከትላንት በስቲያ በመንበረ ፓትርያርኩ አዳራሽ የግማሽ ቀን ስብሰባ በተደረገበት ወቅት፣ የፓትርያርክ አቡነ ማትያስን የመግቢያ ንግግር ተከትለው የተናገሩት ዋና ሥራ አስኪያጁ ብፁዕ አቡነ ማቴዎስ÷ ‹‹አኹን ወደ ስብሰባው ስገባ ነው መልእክቱን የሰማኹት፤ አጀንዳውም ከመቅረቡ በፊት ከቋሚ ሲኖዶሱ ወይም ከእኔ ጋራ ምክክር አልተደረገበትም፤›› በማለት ስብሰባው ከመዋቅሩና ከዕውቅናቸው ውጭ የተጠራ እንደሆነ ተናግረዋል፡፡ የፓትርያርኩ ልዩ ጽ/ቤት ባስተላለፈው የቃል ትእዛዝ መጠራቱ በተገለጸው በዚኹ ስብሰባ÷ የጠቅላይ ቤተ ክህነቱ የመምሪያዎች ዋናና ምክትል ሓላፊዎች፣ የድርጅቶች ዋናና ምክትል ሥራ አስኪያጆች፣ የአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት የአስተዳደር ሓላፊዎች፣ የዋና ክፍሎችና የክፍሎች ሓላፊዎች፣ የክፍላተ ከተማ ቤተ ክህነት ዋናና ምክትል ሥራ አስኪያጆች መሳተፋቸው ተገልጧል፡፡

በ2001 ዓ.ም. በቅ/ሲኖዶስ ውሳኔ በጠቅላይ ቤተ ክህነቱ የመልካም አስተዳደር እንቅስቃሴ መጠናከሩን ተከትሎ የቀድሞው ፓትርያርክ መዋቅሩን ሳይከተሉና ከቅ/ሲኖዶሱ ጋራ ሳይመክሩ ወስደዋቸው ነበር ያሏቸውን ርምጃዎች በመቃወም በወቅቱ የአሜሪካ ሊቀ ጳጳስ የነበሩት የአኹኑ ፓትርያርክ አቡነ ማትያስ በብዙኃን መገናኛ የሰጡት መግለጫ በማስረጃነት ተይዞ እንደሚገኝ ያስታወሱት ዋና ሥራ አስኪያጁ፣ ‹‹ቅዱስነትዎም በምትካቸው ሲቀመጡ መዋቅሩን ሊጠብቁ ይገባል፤ መዋቅሩን ሳይከተሉና ከሚመለከተው አካል ጋራ ሳይመክሩ የሚሠሩት ሥራ ቤተ ክርስቲያኒቱን አደጋ ላይ የሚጥል ነው፤›› እንዳሏቸው ተመልክቷል፡፡

ዋና ሥራ አስኪያጁ ‹‹ውድቀት እንዳይደረስብዎ አማካሪዎችዎ ሊያዝንልዎ ይገባል፤›› ማለታቸውን የገለጹት የስብሰባው ተሳታፊዎች አያይዘውም ‹‹ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ጳውሎስ በአማካሪዎቻቸው ምክንያት ከዕድሜያቸው ዐሥር ዓመት አሳጥረዋል፤ እርስዎም በአማካሪዎችዎ የተነሣ ዕድሜዎ እንዳያጥር ያስቡበት፤›› ሲሉ መምከራቸውን ጠቁመዋል፡፡ ውይይቱን በሰብሳቢነት የመሩት ፓትርያርኩ በበኩላቸው፤ በሥራ የሚያግዛቸው ባለማግኘታቸውና ብቻቸውን በመኾናቸው›› ስብሰባውን ወደ ታች ወርደው ለመጥራት እንደተገደዱ አስረድተዋል፡፡ ፓትርያርኩ ባቀረቡት በጽሑፍ የተደገፈ ገለጻ÷ በቤተ ክህነቱ የመልካም አስተዳደር ዕጦቶች እንዳሉ፣ በሙሰኝነት፣ በዘረኝነትና በአድሏዊነት የሚገለጹ የብልሹ አሠራር ሒደቶች እንደሚታዩ ዘርዝረዋል፡፡ በቤተ ክርስቲያን ስም የሚደራጁ ማኅበራትና ግለሰቦች፣ ሕግና ደንብ እየጣሱ መዋቅሯን እየተፈታተኗት እንደሆነና ከመዋቅራዊ ቁጥጥር ውጭ የሚንቀሳቀስ ሀብትና ንብረት እያካበቱ በመኾኑ አካሔዳቸው ለአንዲት ቤተ ክርስቲያን ጥንካሬና ህልውና ፍጹም አደጋ እንደኾነ አብራርተዋል፡፡

መልካም አስተዳደርን ከማስፈን አንጻር ኹሉም የሥራ ሓላፊዎች ራሳቸውን በመፈተሽና በማጽዳት ችግሩን በዘላቂነት ለማስወገድ በሚደረግ ጥረት የድርሻቸውን እንዲወጡ ያሳሰቡት ፓትርያርኩ፤ የማኅበራት አካሔድ ሥርዓት መያዝ እንዳለበት ጠቁመው ተገቢ ያልሆነውን አካሄድ ኹሉም ሊቃወመው ይገባል ብለዋል፡፡ ‹‹አማካሪዎቼ ዓላማዬን የሚጋሩና የሚያስፈፅሙልኝ ሰዎች ናቸው፤›› ያሉት አቡነ ማትያስ፤ ‹‹አኹንም የምቀጥልበት መኾኑን አሳውቃለኹ›› ብለዋል፡፡ ‹‹ብቻዬን ነኝ፤ በሥራም አልታገዝኹም›› ለሚለው የፓትርያርኩ ንግግር ‹‹ቅዱስነትዎ አዝዘው ምን ያልተፈጸመ ነገር አለ?›› በሚል ምላሽ የሰጡት ዋና ሥራ አስኪያጁ፣ ‹‹ያልተፈጸመ ነገር ካለ ለጉባኤው በይፋ ይገለጽ›› ሲሉ ጠይቀዋቸዋል፡፡ የመልካም አስተዳደር ችግርና የችግሩ መገለጫዎች በርግጥም እንዳሉ ያልሸሸጉት ዋና ሥራ አስኪያጁ፣ መምሪያዎችና ድርጅቶች የበጀት ዓመቱን ዕቅድ በማውጣት፣ የክንውን ሪፖርት በአስተዳደር ጉባኤ በወቅቱ እንዲያቀርቡ፣ ድክመቶች እንዲስተካከሉና ጠንካራ ጎኖች ታቅበው እንዲቀጥሉ መደረጉን በመግለጽ በፓትርያርኩ ጽሑፍ የቀረቡትን መረጃዎች ወቅታዊነት ሞግተዋል፡፡

በልማት ተግባራትና በሠራተኛ አያያዝ ባለፈው በጀት ዓመት የተፈጸሙ ተግባራትን የዘረዘሩት የጽ/ቤቱ ምክትል ሥራ አስኪያጅ ዶ/ር አባ ኃይለ ማርያም መለሰ በበኩላቸው፤ ቀጣይነት ባላቸውና በጥናት በተደገፉ የመልካም አስተዳደር ማሻሻያዎች የሚቀርቡ ቅሬታዎችና የተጉላሉ ባለጉዳዮች አለመኖራቸውን የገለጹ ሲሆን፡፡ የጠቅላይ ቤተ ክህነቱን የፋይናንስ ሥርዐት ዘመናዊው ለማድረግ ዝግጅቱ መጠናቀቁን ጠቁመው የፓትርያርኩን መረጃዎች አግባብነት እንደጠየቁ ታውቋል፡፡ አንድ የስብሰባው ተሳታፊ “አንድ ጣታችንን ወደሌላው ስንጠቁም ሦስቱ ወደኛ እንደሚያመለክት አንዘንጋ” በማለት ፓትርያርኩ ከሙስናና ብልሹ አሠራር ጋር በተያያዘ በዙሪያቸው ስላሉ አማካሪዎችም እንዲያስቡበት ጠቁመዋቸዋል፡፡መንግሥት የሲቪል ማኅበራትን የሚከታተለው ሕግ አውጥቶና ተቋም መሥርቶ መኾኑን፣ በሕጉ የሚተዳደር አብሮ እንደሚጓዝና አልፈልግም ያለ እንደሚወጣ የተናገሩት አቡነ ማቴዎስ፤ ቤተ ክርስቲያን ግን መንፈሳውያን ማኅበራት የሚቋቋሙበት ሕግ እንዳላወጣችና የምታቅፍበት መዋቅር እንዳልዘረጋች ገልጸዋል፡፡

በአገልግሎት ላይ ያሉትን መንፈሳውያን ማኅበራት በሕገ ወጥነትና በመዋቅር ባለመታዘዝ ለመጠየቅ በቅድሚያ ሕጉ ወጥቶ በሥራ ላይ ማዋሉ መቅደም እንዳለበት አስገንዝበዋል፡፡ “ለኢትዮጵያ በረሓ ወርደው፣ ብረት አንሥተው የታገሉትና ዋጋ የከፈሉት ኹሉም ሕዝቦች ናቸው፤ ሕገ መንግሥት ለኹሉም እኩል ነው፤ ለእገሌ ሚኒስትር እናገራለኹ፤ ለእገሌ ደኅንነት እደውላለኹ እያሉ አያስፈራሩን፤›› በማለት ዋና ሥራ አስኪያጁ ፓትርያርኩን እንዳሳሰቧቸው የስብሰባው ተሳታፊዎች ተናግረዋል፡፡ አቡነ ማትያስ ቀደም ሲል ከቋሚ ሲኖዶሱ ጋራ ሳይመክሩ ከአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት የአድባራትና ገዳማት አለቆች ጋራ ባደረጉት ስብሰባ፤ ሊቃነ ጳጳሳቱን ማዘለፋቸውን የጠቀሱት አቡነ ማቴዎስ በዚኽም ኹሉም አባቶች ቅሬታ እንደተሰማቸውና እንዳዘኑባቸው ተናግረዋል፡፡ ፓትርያርኩ ዓመቱን በሙሉ በየደረጃው እቀጥልበታለኹ ባሉት ስብሰባ÷ አጀንዳዎች መዋቅር ሳይጠብቁ፣ ጥናት ሳይደረግባቸውና ሳይብላሉ ውይይቱ ለሚዲያዎች ክፍት መደረጉ ቤተ ክርስቲያኒቷን ለአጉል ትችት ያጋልጣታል ሲሉ ተሳታፊዎች አስተያየት ሰጥተዋል፡፡

             የኢትዮጵያ፣ የግብጽና የሱዳን የውሃ ሚኒስትሮችና ባለሙያዎች የሚሳተፉበትና በታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ ዙሪያ የሚመክረው ሁለተኛው ዙር የሶስትዮሽ የቴክኒክ ውይይት፣ በመጪው ሃሙስና አርብ በካይሮ እንደሚቀጥል የግብጹ አሃራም ድረገጽ ዘገበ፡፡የግብጹን የውሃና የመስኖ ሚኒስትር ሆሳም አልሞሃዚን ጠቅሶ ዘገባው እንዳለው፣ በውይይቱ ላይ የሚሳተፉት 12 የአገራቱ ባለሙያዎች፣ ግድቡ በግብጽና በሱዳን ላይ የሚያደርሰውን ማህበራዊ፣ አካባቢያዊና የውሃ ተጽእኖዎች በተመለከተ ተጨማሪ ጥናት የሚያደርግ አለማቀፍ አማካሪ ኩባንያ ይመርጣሉ ተብሎ ይጠበቃል፡፡

ሚኒስትሩ ከትናንት በስቲያ በሰጡት መግለጫ እንዳሉት፣ ለሁለት ቀናት በሚካሄደው ውይይት ሶስቱ አገራት የግድቡን ተጽዕኖ በተመለከተ ያገኟቸውን አዳዲስ የጥናት ውጤቶች አቅርበው ይወያዩባቸዋል፡፡አገራቱ ባለፈው ነሃሴ በግድቡ ተጽዕኖዎች ዙሪያ የሚሰሩ ተጨማሪ ጥናቶችን በስድስት ወራት ጊዜ ውስጥ ለማጠናቀቅ መስማማታቸውንና የመጀመሪያው ዙር የሶስትዮሽ ውይይት ባለፈው መስከረም 10 ቀን በአዲስ አበባ መካሄዱ ያስታወሰው ዘገባው፣ በውይይቱ የተገኘው ውጤትም በአገራቱ መካከል የተጀመረው ድርድር ወደተሻለ ደረጃ እየተሸጋገረ መሆኑን የሚያመላክት እንደሆነም አክሎ ገልጧል፡፡