Administrator

Administrator

            አለም በቴክኖሎጂ እየረቀቀች ነው፣ የህትመት ኢንዱስትሪውም እጅግ እየዘመነ ነው በሚባልበት በ‘ዘመነ - ኮምፒውተር’፣ ታዋቂው ጋዜጣ ‘ዘ ታይምስ’ 30 አመታትን ወደ ኋላ ተመልሶ ፊቱን ወደ ታይፕ ራይተር ማዞሩን ዘ ኢንዲፔንደንት ዘገበ፡፡ ዘ ታይምስ ጋዜጠኞቹን ለማነቃቃትና በሙሉ ሃይላቸው ሰርተው ዜናዎቻቸውን በተቀመጠላቸው የጊዜ ገደብ እንዲያስረክቡ ለማስቻል ሲል ነው፣ የጋዜጦች ዝግጅት ክፍሎች በዘመናዊ ኮምፒውተሮች ታግዘው በሚሰሩበት በዚህ ዘመን፣ ዘመኑ ያለፈበት የጽህፈት መሳሪያ ወደሚባለው ታይፕ ራይተር ፊቱን ያዞረው፡፡ዘ ኢንዲፔንደንት እንዳስነበበው፣ የጋዜጣው የስራ ሃላፊዎች በዜና ዝግጅት ክፍሉ ውስጥ ግዙፍ የድምጽ ማጉያ ተክለዋል፡፡

ይህ የድምጽ ማጉያ የታይፕ ራይተር ድምጽ የሚያወጣ ሲሆን፣ ድምጹ እየፈጠነ የሚሄድና ጋዜጠኞችን የሚያነቃቃ ነው ተብሏል፡፡ ድንገት በዝግጅት ክፍሉ ውስጥ ተገትሮ ባገኙት የድምጽ ማጉያ ግራ የተጋቡ ጋዜጠኞች እንደነበሩና ከመካከላቸው አንዱም፣ በሚያደምጠው የታይፕ ራይተር ድምጽ በመረበሽ ድምጽ ማጉያውን ለመዝጋት መሞከሩን ዘገባው ገልፃል፡፡ የጋዜጣው የቀድሞ ባልደረባ የነበሩትና በአሁኑ ወቅት ለንደን በሚገኘው ሲቲ ዩኒቨርሲቲ የጋዜጠኝነት መምህር የሆኑት ጆርጅ ብሮክ፣ ዝግጅት ክፍሉ ታይፕ ራይተሮችን መጠቀም ያቆመው እ.ኤ.አ በ1980 ዎቹ እንደነበር አስታውሰው፣ የአሁኑ የታይፕ ራይተር ድምጽ እርግጥም እንደታሰበው ጋዜጠኞችን ለስራ የሚያተጋ መሆንና አለመሆኑን ለመገመት እንደሚያዳግታቸው ገልጸዋል፡፡ የጋዜጣው የዲጂታል ክፍል ምክትል ሃላፊ ሉሲያ አዳምስ በበኩላቸው፣ ነገርዬው አስቂኝ ነው፤ ታይፕ ራይተር ጊዜው ያለፈበት ቢመስልም፣ ቴክኖሎጂ ነውና ሊዘነጋ አይገባም ብለዋል፡፡

(አዋቄ ሞሽሪያ ተ እቸሹ እራሻ መቾ ገውሱ) - የወላይታ ተረት

አንዳንድ ተረቶች በአንድ ወቅት አልደመጥ ሲሉ በሌላ ወቅት ተደግመው መነገራቸው ግድ ይሆናል፡፡

የሚከተለውም እንደዚያው ነው፡፡
ከዕለታት አንድ ቀን ሶስት አህዮች በጠፍ ጨረቃ ሰፊ መስክ ላይ እየጋጡ ሳሉ፤ ሶስት ጅቦች የሚበላ ፍለጋ

ሲዘዋወሩ ያገኙዋቸዋል፡፡
ጅቦቹ ገርሟቸዋል፡፡
አንደኛው ጅብ፤
“እነዚህ አህዮች እንዴት ቢጠግቡ ነው በእኛ ሰዓት፣ በእኛ ግዛት እንደዚህ ተዝናንተው የሚግጡት?”
ሁለተኛው ጅብ
“ዕውነትም የሚገርም ነው፡፡ የተማመኑት ነገር ቢኖር ነው እንጂ እንዲህ ያለ ድፍረት አይፈጽሙም ነበር”
ሦስተኛው ጅብ
“ታዲያ ለምን ችሎት ተቀምጠን አንፈርድባቸውም?” ሲል ሃሳብ አቀረበ፡፡
አህዮቹን ከበቡና ተራ በተራ ሊጠይቋቸው ተሰየሙ፡፡
የመጀመሪያዋን አህያ ጠሩና ጠየቋት፡፡ የማህል ዳኛው ነው የሚጠይቃት፡፡
“እሜቴ አህያ፤ ለመሆኑ በእኛ ሰዓት፣ በእኛ ግዛት፣ በጠፍ ጨረቃ፣ እንዲህ ዘና ብለሽ የምትግጪው ማንን

ተማምነሽ ነው?”
እሜቴ አህያም፤
“አምላኬን፣ ፈጣሪዬን፣ ተማምኜ ነው፡፡ በእኔ ላይ ግፍ የሚሠራን አምላኬ ዝም አይለውም፡፡ መዓት

ያወርድበታል፡፡”
የማህል ጃኛው ጅብም፤
“መልካም ሂጂ፡፡ ፍርድሽን ትሰሚያለሽ፡፡ ሌላዋን ጥሪያት”
ለሁለተኛዋ አህያም ጥያቄው ቀረበላት:-
“አንቺስ ማንን ተማምነሽ ነው በጠፍ ጨረቃ፣ በእኛ ሰዓት፣ በእኛ ግዛት
ፍንጥዝጥዝ ብለሽ የምትግጪው?”
ሁለተኛይቱ አህያም፤
“ጌታዬን፣ አሳዳሪዬን ተማምኜ ነው፡፡ በእኔ ላይ ጥቃት የሚያደርስን ማንንም ቢሆን ጌታዬ ዝም አይለውም፡፡

ይበቀልልኛል ብዬ በማመን ነው” ስትል መለሰች፡፡
ማህል ዳኛው ጅብ፤
“መልካም፡፡ አንቺም ፍርድሽን ትሰሚያለሽ፡፡ ሌላዋን ጥሪያት” አላት፡፡
ሦስተኛይቱ ቀረበች፡፡
ማህል ዳኛው ጅብም፤
“አንቺስ ማንን ተማምነሽ ነው ይሄ ሁሉ መዝናናት?” አላት
ሦስተኛይቱ አህያም፤
“እናንተን፣ እናንተን፣ የአካባቢውን ገዢዎች ተማምኜ ነው ጌቶቼ”
ዳኛውም፤
“መልካም፡፡ ሁላችሁም ፍርዳችሁን ጠብቁ” አሉና ሸኟት፡፡
ዳኞቹ መምከር ጀመሩ፡፡
ግራ ቀኝ ዳኞች አስተያየት ከሰጡ በኋላ፤ የመካከል ዳኛው ጅብ እንዲህ አሉ :-
“የመጀመሪያዋን ብንበላት እንዳለችው አምላክ አይለቀንም፡፡ ይበቀልላታል፡፡ ሁለተኛዋን ብንበላት ምናልባት

አሳዳሪ ጌታዋ ተከታትሎ፣ ያጠፋናል፡፡ ይቺን ሶስተኛዋን፣ እኛን የተማመነችውን ብንበላት ማናባቱ ይጠይቀናል?”

ሲል መሪ - ሀሳብ አቀረበ፡፡
ሁለቱ ጅቦች ባንድ ድምጽ፤
“ዕውነት ነው፡፡ እኛን የተማመነችውን እንብላት!” አሉ፡፡
እነሱን የተማመነችው ላይ ሰፈሩባት፡፡
***
የጌቶች አስተሳሰብ ምን እንደሚመስል ተገዢ ወዳጆች ማወቅ አለባቸው፡፡ ሎሌነቱንም በቅጥ በቅጥ አለመያዝ፣

የመጨረሻውን ቀን ከማፋጠን አያልፍም፡፡ “የምጣዱ እያለ የእንቅቡ ተንጣጣ የሚለውን ተረት፤ በአፉ የሚንጣጣ

ሁሉ በጊዜ ሊገነዘብ ይገባል፡፡ መጨረሻው፤ “ያመኑት ፈረስ፣ ይጥል በደንደስ” ነውና፡፡ “እናቴን ያገባ ሁሉም

አባቴ ነው” ለሚሉ የዋሀን ሁልጊዜ ፋሲካ ሊመስላቸው ቢችልም፤ ለሁሉም ጊዜ አለውና “ምነው ምላሴን

በቆረጠው” የሚያሰኝ የፍርድ ቀን እንደሚኖር አሌ አይባልም፡፡
“እንብላም ካላችሁ እንብላ፤ አንብላም ካላችሁ እንብላ” በሚል ጅባማ ፍልስፍና ውስጥ መበላላት መሪ መርሀ -

ግብር መሆኑን ለአፍታም መዘንጋት የለበትም፡፡
“ለጋማማ አህያም ጋማ አላት
አያስጥልም እንጂ ጅብ ሲዘነጥላት” ሲባል የከረመው ያለ ነገር አይደለም፡፡
“እነሆ ብዙ ዘመን አለፍን፡፡ ከሁሉም የተረፈን ብዙ ምላሶችና እጅግ ጥቂት ልቦች ናቸው” ይላል ሲ ጆርጅ

የተባለ ፀሐፊ፡፡ በሀገራችን በቅንነት ሃሳብ የሚሰጡና በሎሌነት ሃሳብ የሚሰጡ መለየት አለባቸው፡፡ “ውሸት

አለምን ዞሮ ሊጨርስ ሲቃረብ ዕውነት ገና ቦት ጫማውን እያጠለቀ ነው” መባሉ በምክን እንጂ በአቦ - ሰጡኝ

አይደለም፡፡ በየአገሩ፤ የንጉሥ አጫዋቾች የተለያዩ ናቸው፡፡ አንድ የጋራ ባህሪ ግን አላቸው - ንጉሱ ሲያስነጥሱ

ማስነጠስ፡፡ አድር ባይነት፡፡ በመካያው ራሱ አድርባዩ ማንነቱ ይጠፋበትና “የዘሬን ብለቅ ያንዘርዝረኝ” ማለት

እንኳን ይሳነዋል፡፡ “ነገር አንጓች፤ እንኳን ለጌታው ለራሱም አይመች” ነውና ፍፃሜው አጓጉል መሆኑ ዕሙን

ነው፡፡
የትዕዛዝ ሁሉ ጉልላት ለህሊና መታዘዝ ነው፡፡ ማንም ቢሆን ማን፤ ህሊናውን ሲክድ
አታላይ መሆኑ አይቀሬ ነው፡፡ ብልጥ ለማኝ፤ “ጌታዬ ጌታዬ አምና የሰጡኝን ልብስ አምስት ዓመት ለበስኩት”

እያለ ይኖራል፡፡ በዕውቀት ያልተደገፈ ድፍረት፣ የህሊና ማጣት ምርኩዝ ነው፡፡” ወትሮም፤ “መራዡ ተኳሹ” ሲል

የኖረ፣ “በራዡ ከላሹ” ማለት ከጀመረ ሁለተዜ ጥፋት ነው፡፡ ሀገራችን አያሌ አድር - ባይ አይታለች፡፡ ለሀገራችን

ጐታቿም አጥፊዋም፣ “አሾክሿኪው” ነው፡፡ ከታሪክ መማር ዕርም በሆነባት አገር ቀለሙን እየለዋወጠ አድር -

ባይ ሁሉ እየመጣ፤ “እንቅፋት በመታው ቁጥር ቲዎሪ ድረሽ” (ያውም ዕውነተኛ ቲዎሪ ካለው) እያለ፤ “መንገድ

ባስቸገረው ቁጥር” መመሪያ ማሪኝ” እያለ ህሊናውን እየሸጠ ይኖራል፡፡ ልባም አይደለምና አፍ ያወጣል፡፡ ምላሱ

እየረዘመ፣ አንጐሉ እየጨለመ ይሄዳል፡፡ አበው “ከመሃይም ምላስ ይሰውረን” የሚሉት ለዚህ ነው፡፡ ማህታማ

ጋንዲ እንግሊዝን “በመጨረሻ ባዶህን ትወጣታለህ!” ማለቱን አንርሳ፡፡
“ቅዳሴው ሲያልቅበት ቀረርቶ አከለበት” እንዲሉ በምላሱ የሚተዳደር ሰው ውሸት ማብዛቱ ግዱ ነው፡፡ ዕውቀተ

- ቢስ መሠረቱ ለዕውነት ረሃብ ያጋልጠዋልና! “አፈኛ ሴት፤ የአምስት ዳኛ ሚስት ነኝ፤ ትላለች” የሚለው

የወላይታ ተረት ኢላማ ይሆናል!!
መልካም የመስቀል በዓል!

 “የደሞዝ ጭማሪው ለሌላው ሲደርስ ለጋዜጠኛው አልደረሰም” ጋዜጠኞች

“ጭማሪው ሰሞኑን በቦርዱ ተወስኗል፤ በቀጣዩ ወር ይደርሳቸዋል” አቶ ሽመልስ ከማል

 

“ድርጅቱ በደመነፍስ ይመራል የሚለው አጉል አሉባልታ ነው” የፕሬስ ድርጅት ሥ/አስኪያጅ

በኢትዮጵያ ፕሬስ ድርጅት ስር የሚታተሙት አዲስ ዘመን፣ ኢትዮጵያን ሄራልድ፣ በሪሳ እና አል-አለም ጋዜጠኞች በመስሪያቤታቸው የመልካም አስተዳደር እጦት እየተማረሩ መሆኑን ገለፁ፡፡ መንግስት በድርጅቱ ውስጥ ያለውን ዘርፈ ብዙ ችግር እያወቀ ምላሽ አለመስጠቱ እንዳሳዘናቸው ጋዜጠኞቹ ተናግረዋል፡፡ ሌላው ቀርቶ ለመንግስት ሰራተኞች የተደረገው የደሞዝ ጭማሪ ለጋዜጠኞች አለመድረሱን የገለፁት ሰራተኞቹ፤ ላለፉት አራት ዓመታት የቦርድ ሰብሳቢ ሆነው እያገለገሉ ያሉት አቶ ሽመልስ ከማል አንድም ቀን ሰብስበው አወያይተዋቸው እንደማያውቁ በምሬት ገልፀዋል፡፡

“ድርጅቱ በዚህ ዓመት ይህን እሰራለሁ ብሎ ያስቀመጠው ግብ የለም፣ ጋዜጠኛው የሚመራው ብቃት በሌለው ስራ አስኪያጅ ነው፣ ይህንንም በስብሰባ ለራሳቸው ለስራ አስኪያጁ ተናግረን ችግሩን የሚያጣራ ኮሚቴ ተቋቁሞ ያጣራውን ለሚመለከተው አካል ቢያቀርብም የተሰጠ ምላሽ የለም” ብለዋል - ጋዜጠኞቹ፡፡ የቦርዱ ሰብሳቢ የመንግስት ኮሙኒኬሽን ጽ/ቤት ሚኒስቴር ዴኤታ አቶ ሽመልስ ከማል በበኩላቸው፤ አንድም ቀን አወያይቶን አያውቅም የሚለው ፍፁም ሀሰትና የተሳሳተ መረጃ መሆኑን ገልጸው፣ በየጊዜው ከጋዜጠኞችና ከኤዲተሮች ጋር እንደሚወያዩና በኤዲተሮችና ዋና አዘጋጆች ፎረም ላይ የተለያዩ ሃሳቦች እየተነሱ በምክክር እንደሚሰሩ ተናግረዋል፡፡

“ከሰራተኛው መካከል የራሳቸው ጥቃቅን የጥቅም ግጭት ያላቸው አንዳንድ ግለሰቦች የሚነዙት አሉባልታ እንደ አጠቃላይ የሰራተኛው ችግር ተደርጎ መነሳቱ መሰረተ ቢስ ነው” ብለዋል - አቶ ሽመልስ፡፡ የኢትዮጵያ ፕሬስ ድርጅት ዋና ስራ አስኪያጅ አቶ ሰብስቤ ከበደን በጉዳዩ ዙሪያ አነጋግረናቸው በሰጡት ምላሽ “ድርጅቱ በእቅድና በፕሮግራም እንደሚመራ በቢሮ ተገኝቶ አሰራሩን ማረጋገጥ ይቻላል” ያሉ ሲሆን፣ አንዳንድ የግል ችግር ያለባቸው ግለሰቦች የድርጅቱንና የአመራሩን ስም ለማጥፋት ሆን ብለው የሚነዙት ተጨባጭ ያልሆነ ወሬ እንደሆነ ተናግረዋል፡፡ ድርጅቱ ችግር ቢኖርበት ኖሮ ሰራተኛውን የሚያወያይበት የስብሰባ መድረክ እያዘጋጀ አያወያይም ነበር” ያሉት ሥራ አስኪያጁ፤ በቅርቡ አጠቃላይ ስብሰባ ተጠርቶ ከሰራተኞች የተለያዩ አስተያየቶች መሰጠታቸውንና በውይይት መድረኩ ላይ የተነሱትን አንዳንድ ክፍተቶች እንደግብአት በመጠቀም የአሰራር ማስተካከያ እየተደረገ እንደሆነ ለአዲስ አድማስ ገልፀዋል፡፡

ጋዜጠኞቹ በበኩላቸው ለመልካም አስተዳደር እጦቱ እንደዋና ማሳያ ያቀረቡት የድርጅቱ ህንፃ በሁለት ዓመት ተገንብቶ ይጠናቀቃል ቢባልም አራት አመት ፈጅቶ እንኳን አሁንም ይቀረዋል፣ የሰራተኛ የቅጥር ሁኔታው ግልፅነት የለውም፣ ሹፌር ሳይቀር በፍሪላንስ የሚቀጠርበት ሁኔታ አለ፣ የደሞዝ ጭማሪና የእድገት ሁኔታ በአድሎአዊ አሰራር የተተበተበ ነው፤ በዚህም የተነሳ ለጋዜጦቹ አለኝታ የሚባሉ ወደ 50 ሰራተኞች ባለፈው ዓመት ለቀዋል፤ ዘንድሮም የለቀቁ አሉ በማለት ተናግረዋል፡፡ መንግስት ይህን ሁሉ ችግር ያውቃል፤ ግን ማስተካከያ አልተደረገም ብለዋል፡፡ ፕሬስ ውስጥ በሲቪል ሰርቪስና በቦርድ የሚተዳደር ሁለት ዓይነት ሰራተኛ መኖሩን ጋዜጠኞቹ ገልጸው፣ በሲቪል ሰርቪስ የሚመራው ሰራተኛ ጭማሪው ሲደርሰው የእኛ ዘግይቷል ብለዋል፡፡

“በአንድ ወቅት ከኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት ድርጅት ጋዜጠኞች ደሞዝ የፕሬሱ ጋዜጠኞች ይበልጥ ነበር” ያለው አንድ ቅሬታ አቅራቢ ጋዜጠኛ፤ ኢዜአዎች ፕሬስ አቻ ድርጅት ሆኖ እንዴት ደሞዝ ይበልጡናል በሚል ላነሱት ጥያቄ በአፋጣኝ ምላሽ ተሰጥቷቸው ደሞዛቸው መስተካከሉን አስታውሶ፤ የእኛ አቻ ድርጅት በሆነው የኢትዮጵያ ብሮድካስቲንግ ኮርፖሬሽን (EBC) በቅርቡ እስከ 200 ፐርሰንት የደሞዝ ጭማሪ ቢደረግም በእኛ ድርጅት ምንም የተባለ ነገር ባለመኖሩ ጋዜጠኛው በድርጅቱ ተስፋ እየቆረጠ ነው ብሏል፡፡ የኢትዮጵያ ፕሬስ ድርጅት ስራ አስኪያጅ ጭማሪውን በተመለከተ በሰጡት ምላሽ፤ በሲቪል ሰርቪስ የሚተዳደሩት የሚከፈላቸው በመንግስት በመሆኑ እንደማንኛውም የመንግስት ሰራተኛ ጭማሪው ቀድሞ እንደረሳቸው አምነው፣ ሆኖም በቦርድ ለሚተዳደሩት ጋዜጠኞች የሚከፈለው ድርጅቱ ከማስታወቂያና ከጋዜጣ ሽያጭ ከሚያገኘው ገቢ ላይ በመሆኑና ስኬሉ ስለሚለያይ ቦርዱ ተወያይቶ ውሳኔ እስኪሰጥበት ሲጠበቅ እንደነበር አብራርተዋል፡፡ “ውይይቱ ተጠናቅቆ ቦርዱ ከትላንት በስቲያ ስለወሰነላቸው ጭማሪው በቀጣዩ ወር ይደርሳቸዋል” ብለዋል - ሥራ አስኪያጁ፡፡

በስብሰባው ላይ የአመራር ብቃት የለዎትም፤ ቦታውን ይልቀቁ በሚል ከጋዜጠኞች ቅሬታ ስለመቅረቡ አቶ ሰብስቤን ጠይቀናቸው፤ “እኔ ስብሰባ ላይ እንዲህ የሚባል ትችት አልቀረበብኝም” ያሉት አቶ ሰብስቤ፤ እርግጥ በስነ-ምግባርም ሆነ በእውቀት ብቃት የሌለው አንድ ጋዜጠኛ “ቦታውን ልቀቅ” ብሎ በግል ተናግሮኛል፤ ጋዜጠኛው አሁን ስራ ለቋል” ብለዋል፡፡ ብዙ ጋዜጠኞች ከድርጅቱ ይለቃሉ ስለሚባለው አንስተንባቸው በሰጡት ምላሽ፤ “ከጥቅማጥቅም ጋር በተያያዘ ጋዜጠኞች ይለቃሉ፣ የተሻለ ደሞዝ ሲያገኙ የትኛውም መ/ቤት እንደሚልቁት ሁሉ እዚህም ይለቃሉ፤ በዚያው ልክ እኛም እንቀጥራለን” ብለዋል፡፡ ሰራተኞቹ፤ የመልካም አስተዳደር ችግሩ በአስቸኳይ ካልተቀረፈ፣ እንደአቻ ድርጅት ማግኘት የሚገባንን የደሞዝ እድገት ካላገኘንና አድሎአዊ አሰራር ካልቀረ ድርጅቱን ለመልቀቅ እንገደዳለን ሲሉ አሳስበዋል፡፡ ዋና ሥራ አስኪያጁ በበኩላቸው፤ በድርጅቱ ውስጥ መሻሻሎችን ለመፍጠርና ወደ ኮርፖሬት አደረጃጀት ለመቀየር ስራዎች ተሰርተው በመጠናቀቅ ላይ ናቸው ብለዋል፡፡

              የአፍሪካ የጋዜጠኞች ፌዴሬሽን የኢትዮጵያ መንግስት በእስር ላይ የሚገኙ ጋዜጠኞችን እንዲፈታና በቅርቡ አገራቸውን ጥለው የተሰደዱ ጋዜጠኞችም፣ ወደ አገር ቤት ተመልሰው ስራቸውን የሚቀጥሉበትን ምቹ ሁኔታ እንዲፈጥር ጠየቀ፡፡ አለማቀፉ የጋዜጠኞች ፌዴሬሽን ባለፈው ረቡዕ በሰጠው ጋዜጣዊ መግለጫ፤ በኢትዮጵያ የሚታየው የፕሬስ ነጻነት ጥሰት፣ የጋዜጠኞች እስርና ስደት ያሳስበኛል ብሏል፡፡ “በኢትዮጵያ የፕሬስ ነጻነትን የሚጥሱ ተግባራት መከናወናቸው መቀጠሉ እንዲሁም የሚታሰሩና አገር ጥለው የሚሰደዱ ጋዜጠኞች ቁጥር ከጊዜ ወደ ጊዜ እየጨመረ መምጣቱ ያሳስበናል” ያሉት የአፍሪካ የጋዜጠኞች ፌዴሬሽን ፕሬዚዳንት ሞሃመድ ጋርባ፤ የኢትዮጵያ መንግስት ከመገኛኛ ብዙሃን ጋር ሃቀኛ ውይይትና ምክክር በማድረግ፣ ራሳቸውን ተቆጣጥረው በአግባቡ እንዲንቀሳቀሱ ምቹ ሁኔታዎችን እንዲፈጥር ጥያቄ ማቅረባቸውን ገልጸዋል፡፡በኢትዮጵያ ብሄራዊ ጋዜጠኞች ህብረትና በምስራቅ አፍሪካ የጋዜጠኞች ማህበር አዘጋጅነት በቅርቡ በአዲስ አበባ በተካሄደው የምርመራ ጋዜጠኝነት አውደ-ጥናት ላይ የተሳተፈውና ከምስራቅ አፍሪካ የጋዜጠኞች ማህበርና ከአለማቀፉ የጋዜጠኞች ፌዴሬሽን የተወከሉ 3 አባላት ያሉት የልኡካን ቡድን፣ ከመንግስት የኮሙኒኬሽን ጉዳዮች ሚኒስትር አቶ ሬድዋን ሁሴን ጋር በጉዳዩ ዙሪያ መምከሩንም የፌዴሬሽኑ መግለጫ አስታውሷል፡፡

ከአካባቢው አገራት በበለጠ ሁኔታ ጋዜጠኞች የሚታሰሩትና የሚሰደዱት በኢትዮጵያና በኤርትራ እንደሆነ ለሚኒስትሩ የገለጹት የልኡካን ቡድኑ አባላት፣ የኢትዮጵያ መንግስት በእስር ላይ የሚገኙትን ሁሉንም ጋዜጠኞች እንዲፈታና በስደት የሚገኙትም ወደአገራቸው የሚመለሱበትን ሁኔታ እንዲያመቻች መጠየቃቸውን ጠቁሟል፡፡ አቶ ሬድዋን በበኩላቸው ለልኡካን ቡድኑ በሰጡት ምላሽ፣ በቅርቡ አገር ጥለው የተሰደዱት ጋዜጠኞች ክስ እንዳልተመሰረተባቸውና ከአገር የሚያስወጣቸው ምክንያት እንደሌለ ፤ የአገሪቱ መንግስትም ሃሳብን የመግለጽ ነጻነትን ለማስከበር ቁርጠኛ አቋም ይዞ እየሰራ እንደሚገኝ መናገራቸውን መግለጫው አመልክቷል፡፡ የአፍሪካ የጋዜጠኞች ፌዴሬሽን በ40 የአህጉሪቱ አገራት ውስጥ የሚገኙ ከ50ሺህ በላይ ጋዜጠኞችን እንደሚወክል፣ አለማቀፉ የጋዜጠኞች ፌዴሬሽን ባወጣው መግለጫ አስታውቋል፡፡

      ሆቴሉ የብድርና የኮንትራት ማናጅመንት ስምምነቶችን ነገ ይፈራረማል

ግንባታው ከ18 ወራት በኋላ ተጠናቆ አገልግሎት መስጠት ይጀምራል የተባለው የአለማቀፉ ኢንተርኮንቲኔንታል ግሩፕስ አካል የሆነው “ክራውን ፕላዛ ሆቴል”፤ በአዲስ አበባ በአገልግሎት ላይ ከሚገኘው “ክራውን ሆቴል” የስያሜ ኮፒ ራይት መብት ጥያቄ ቀርቦበት ፍ/ቤት የንግድ ስያሜ እግድ አስተላልፎበታል፡፡ “ክራውን” የሚለው ስያሜ በኢትዮጵያ አዕምሯዊ ንብረት ፅ/ቤት የተመዘገበና በስራ ላይ የሚገኝ እንደሆነ የጠቆመው “ክራውን ሆቴል”፤ ስያሜው ለሌላ አካል መሰጠቱ ተገቢ አይደለም ሲሉ ለፍ/ቤቱ ይግባኝ ብሏል፡፡ “ክራውን ሆቴል” የሚለው የንግድ ምልክት በኢትዮጵያ አዕምሯዊ ንብረት ፅ/ቤት ተመዝግቦ አገልግሎት መስጠት ከጀመረ ከ20 አመታት በላይ አስቆጥሯል የሚለው ለይግባኝ ሰሚ ፍ/ብሔር ችሎት የቀረበው የሆቴሉ ማመልከቻ፤ ውሳኔው “ክራውን ሆቴል” በሁለት አስርት ዓመታት ያገኘውን ስምና ዝና እንዲሁም ገበያውን አዲሱ ሆቴል እንዲሻማበት የሚያደርግ ነው ብሏል፡፡

የኢትዮጵያ አዕምሯዊ ንብረት ጽ/ቤት “ክራውን ሆቴልን” ሳያማክር ሚያዚያ 28 ቀን 2006 ዓ.ም የዓለም አቀፍ ኢንተርኮንቲኔንታል ፕሩፕስ አካል ሆነው ሆቴል “ክራውን ፕላዛ” የሚለውን ስያሜ መፍቀዱ አግባብ አይደለም ሲል ይግባኝ የጠየቀው ክራውን ሆቴል፤ ፍ/ቤቱ አዕምሯዊ ንብረት ፅ/ቤት የሰጠው ውሳኔ የይግባኝ ባይን በንግድ ምልክቱ የመጠቀም ህጋዊ መብት በእጅጉ የጎዳ መሆኑን ፍ/ቤቱ ተገንዝቦ የፅ/ቤቱን ውሳኔ ሙሉ በሙሉ በመሻር ስሙ በድጋሚ የተሰጠው ሆቴል “ክራውን ፕላዛ” በሚለው የንግድ ምልክት መጠቀም አይችልም የሚል ውሳኔ እንዲሰጥለት በሰኔ 23 ቀን 2006 ዓ.ም ለፍ/ቤቱ በፅሁፍ አመልክቶ ነበር፡፡ ፍ/ቤቱም መስከረም 7 ቀን 2007 ዓ.ም በዋለው ችሎት፤ ይግባኝ ባይ መስከረም 5 ቀን 2007 ዓ.ም በቃለ መሃላ በተደገፈ አቤቱታ እግድ መጠየቃቸውን አስታውቆ በሰጠው ትዕዛዝ፤ ሌላ ተለዋጭ ትዕዛዝ እስኪሰጥ ድረስ የኢትዮጵያ አዕምሯዊ ንብረት ፅ/ቤት የሰጠው ውሳኔ አፈፃፀም ታግዷል ብሏል፡፡

የይግባኝ ቅሬታውን ለመስማትም ለጥቅምት 12 ቀን 2007 ዓ.ም ተለዋጭ ቀጠሮ ሰጥቷል፡፡ በጉዳዩ ላይ ያነጋገርናቸው በኢትዮጵያ አዕምሯዊ ንብረት ፅ/ቤት የንግድ ምልክትና ኢንስፔክሽን ዋና የስራ ሂደት ጊዜያዊ ዳይሬክተር አቶ ደረጀ ፅጉ፤ የፍ/ቤቱ እግድ ትዕዛዝ እንደደረሳቸው አረጋግጠው፣ ጉዳዩ በፍ/ቤት የተያዘ በመሆኑ ምንም አይነት አስተያየት መስጠት እንደማይችሉ፣ ነገር ግን ጽ/ቤታቸው የፍ/ቤቱን እግድ እንደሚያስከብር ገልፀዋል፡፡ አለማቀፍ የሆኑ የሆቴልም ሆነ ሌሎች ኩባንያዎች ስያሜና የንግድ አርማ የሃገራችን ኩባንያዎች በምን አግባብ ነው እንዲጠቀሙ የሚደረገው ስንል የጠየቅናቸው ዳይሬክተሩ፤ “ባለ ኩባንያው የንግድ ምልክቱን ያስመዘግባል፤ በንግድ ምልክቱ ዙሪያም ተቃዋሚ ካለ እንዲቀርብ የጋዜጣ ማስታወቂያ ይወጣል፤ ካልቀረበና በምርመራ ከተረጋገጠ ይሰጠዋል፤ በዚህ መንገድ ነው የሚስተናገደው” ብለዋል፡፡ በሌላ በኩል የስትራክቸር ግንባታ ስራው ሙሉ ለሙሉ መጠናቀቁ የተገለጸው “ክራውን ፕላዛ ሆቴል”ን የሚያስገነባው ፀሜክስ ሆቴሎችና ቢዝነስ ኃ/የተ/የግ ማህበር ከአለም ባንክ ጋር የ19 ሚሊዮን ዶላር የብድር ስምምነት የሚፈራረም ሲሆን በፀሜክስ እና በኢንተርኮንቲኔንታል ሆቴል ግሩፕ መካከል ደግሞ የሆቴል ማናጅመንት ኮንትራት ውል ስምምነት በነገው ዕለት ይፈራረማል ተብሏል፡፡

                  የ4.5ቢ. ዶላር ድጋፍ አድርገዋል የኩዌት አሚር የተከበሩ ሼክ ሳባህ አል-አህመድ አል-አልጃበር አል-ሳባህ ሃይማኖትና ጎሳ ሳይለዩ ለዓለም ህዝብ ባደረጉት የተለያዩ ድጋፎች የተባበሩት መንግስታት ድርጅት (ተመድ)፣ “የሰብአዊ በጎ አድራጎት ስራዎች መሪ” በማለት እንደሸለማቸው የኩዌት አምባሳደር አስታወቁ፡፡ በኢትዮጵያ፣ በአፍሪካ ህብረትና በዩጋንዳ የኩዌት አምባሳደር ሺድ አልሃጅሪ፣ በጽ/ቤታቸው ለጋዜጠኞች በሰጡት መግለጫ፣ አሚሩ ሊሸለሙ የቻሉት፣ ባላቸው መልካም አመለካከትና ቅን አስተሳሰብ የህዝቦችን ህይወት ወደተሻለ ደረጃ ለማድረስና በተለያዩ ችግሮች ውስጥ ያሉ ህዝቦችን ለመርዳት ያደረጉትን ሰብአዊ ስራ ለማጉላትና እውቅና ለመስጠት መሆኑን ገልጸዋል፡፡

አሚሩ ያደረጉት ሰብአዊ ድጋፍ 4.5 ቢሊዮን ዶላር መድረሱን አምባሳደሩ ጠቅሰው፣ 2.5 ቢሊዮን ዶላሩ የአፍሪካ ድርሻ ነው ብለዋል፡፡ ጥቃቅንና መካከለኛ ቢዝነሶች ለመደገፍና ለማበረታታት 500 ሚሊዮን ዶላር፣ ምስራቃዊ ሱዳንን እንደገና ለመገንባት 100 ሚሊዮን ዶላር፣ ለፍልስጤም ስደተኞች ድጋፍ 34 ሚሊዮን ዶላር፣ ለአፍሪካ ህብረት የጤና ክሊኒክ ማስፋፊያ 5 ሚሊዮን ዶላር፣ በአፍሪካ ለሚደረጉ የልማት ፕሮጀክቶች 1 ቢሊዮን ዶላር፣ በአፍሪካ ለሚደረጉ ኢንቨስትመንቶች 1 ቢሊዮን ዶላር ድጋፍ ያደረጉ ሲሆን በአጠቃላይ ለ13 የሰብአዊ በጎ አገልግሎት ሥራዎች 4.5 ቢሊዮን ዶላር ድጋፍ መስጠታቸው ታውቋል፡፡ ስለኢትዮጵያና ኩዌት ግንኙነት የተጠየቁት አምባሳደሩ፤ የሁለቱ አገሮች ግንኙነት ረዥም ዘመን ያስቆጠረ መሆኑን ጠቅሰው፣ የቀድሞው ጠቅላይ ሚ/ር መለስ ዜናዊ ግንኙነቱን ከፍተኛ ደረጃ ላይ እንዳደረሱት በማስታወስ አሁን በስልጣን ላይ ያሉት ጠቅላይ ሚ/ር ኃይለማርያም ደሳለኝ ግንኙነቱ እንዲቀጥል ባደረጉት ጥረት፣ ሁለቱ አገራት 14 የሁለትዮሽ ስምምነቶች መፈራረማቸውን ገልፀዋል፡፡ በኩዌት ባሉ ኢትዮጵያውያን ላይ የሚፈፀሙ ጥቃቶችን በተመለከተ መንግስታቸው ምን እርምጃ እንደወሰደ ተጠይቀው በሰጡት ምላሽ፤ “ኩዌት በህግ ተቋም የምትተዳደር አገር ስለሆነች፣ ፖሊስና ፍርድ ቤቶች ህጉን ለማስከበር በከፍተኛ ሁኔታ ይሰራሉ፤ የኩዌት ህግ ለማንም አያደላም፤ የአገሩም ሆነ የውጭ ዜጎች እኩል ነው የሚዳኙት፡፡” ብለዋል አምባሳደር ራሺድ አልዛድሪ፡፡ በኩዌት 80ሺ የሚደርሱ ኢትዮጵያውያን እንደሚኖሩ ይታወቃል፡፡

             ታዋቂው ፎርብስ መጽሄት ከኒውዮርክ አፍሪካን ሬስቶራንት ዊክ ጋር በመተባበር ባወጣው በኒውዮርክ ሲቲ የሚገኙ ምርጥ አስር የአፍሪካውያን ሬስቶራንቶች ዝርዝር ውስጥ፣ የኢትዮጵያውያኑ ሬስቶራንቶች ‘ንግስተ ሳባ’ እና ‘ባቲ’ ተካተቱ፡፡ በኒውዮርክ ሲቲ የአፍሪካውያን ምግቦችን በማቅረብ ከሚታወቁት ከ50 በላይ ሬስቶራንቶች መካከል፣ በሚያዘጋጇቸው ምግቦች ጣዕም፣ በመስተንግዶ፣ በውስጣዊ ድባብና ዘላቂነት በሚሉ መስፈርቶች ከተመረጡት 10 ሬስቶራንቶች መካከል የኤርትራውያኑ ‘ምጽዋ’ም ይገኝበታል፡፡

ከታዋቂው ታይምስ አደባባይ በቅርብ ርቀት ላይ የሚገኘውና በሼፍ ፊሊጶስ መንግስቱ ባለቤትነትና አስተዳዳሪነት የሚመራው ንግስተ ሳባ፣ የኢትዮጵያውያንን ባህላዊ ምግቦች እያጣጣሙ ከወዳጅ ዘመድ ጓደኛ ጋር ለመጨዋወት ተመራጭ ቦታ እንደሆነ የገለጸው ፎርብስ፤ የሚያቀርበው ጣፋጭ ኬክም ልዩ መገለጫው እንደሆነ ጠቁሟል፡፡ በባህላዊ የቤት ማስጌጫዎች የተዋበው ይሄው የኢትዮጵያውያን ሬስቶራንት፤ በተለያዩ የአሜሪካ የቴሌቪዥን ፕሮግራሞች ላይ የዘገባ ሽፋን እንዳገነ ፎርብስ አስታውሷል፡፡ በአዲስ አበባ በተወለደችው ህብስት ለገሰ ባለቤትነት የሚንቀሳቀሰው ባቲም፣ ጣፋጭ የኢትዮጵያውያን ምግቦችን በአስደናቂ መስተንግዶ ለደንበኞቹ በማቅረብ እንደሚታወቅ ፎርብስ ገልጿል፡፡ የሴኔጋሎቹ “ፖንቲ ቢስትሮ”፣ “ካፌ ሪዮ ዲክስ” እና “ሌኖክስ ሳፋየር”፣ የደቡብ አፍሪካዎቹ “ማዲባ” እና “ቶላኒ ኢተሪ ኤንድ ዋይን”፣ የናይጀሪያው “ቡካ” እንዲሁም የአይቬሪኮስቱ “ፋራፊና ካፌና ላውንጅ”ም፣ በኒውዮርክ ሲቲ ምርጥ 10 የአፍሪካውያን ሬስቶራንቶች ዝርዝር እንደተካተቱ ለማወቅ ተችሏል፡፡

በአዲስ አበባና በአምስት ክልሎች ባቋቋሟቸው የፌስቱላ ሆስፒታልና የህክምና ማዕከላት ከ40ሺህ በላይ ለሚሆኑ ታማሚዎች የህክምና እርዳታ በመስጠት የሚታወቁት የዶ/ር ካትሪን ሃምሊን 90ኛ ዓመት የልደት በዓል፣ ዛሬ በዋሽንግተን ዲሲ ሪትዝካርልተን ይከበራል፡፡ የፕሮግራሙን አዘጋጆች በመጥቀስ ታዲያስ መጽሄት ከኒውዮርክ እንደዘገበው፣ ዶ/ር ሃሚሊን በስነ-ስርዓቱ ላይ ተገኝተው ልዩ መልዕክት እንደሚያስተላልፉና በወሊድ ምክንያት የሚፈጠሩ የጤና ችግሮችን ለማጥፋት ርብርብ እንዲደረግ ያስተላለፉትን ጥሪ ተቀብለው የራሳቸውን ድጋፍ ለማድረግ የሚፈልጉ በርካታ ታዋቂ ግለሰቦችና ጥሪ የተደረገላቸው እንግዶች ዝግጅቱን እንደሚታደሙ ይጠበቃል፡፡ የዶ/ር ሃምሊን የ90ኛ አመት የልደት በዓል፣ የተከበሩ ቀዳማዊት እመቤት ሮማን ተስፋዬን ጨምሮ ከአገር ውስጥና ከሌሎች የአለም አገራት የተጋበዙ እንግዶች በተገኙበት ባለፈው ጥር ወር በአዲስ አበባ መከበሩን የጠቆመው ዘገባው፤ ዶ/ር ሃምሊን ፌስቱላን ከኢትዮጵያ ለማጥፋት ላለፉት 55 አመታት ከፍተኛ ጥረት ሲያደርጉ መቆየታቸውን አስታውሷል፡፡ በአዲስ አበባና በክልሎች የፌስቱላ ሆስፒታልና የህክምና መስጫ ማዕከላትን በማቋቋም በአገሪቱ ከፍተኛ የጤና ችግር ሆኖ የቆየውንና ተገቢ ህክምና ያልነበረውን ፌስቱላን ለማጥፋት ይዘው ለተነሱት ታላቅ ራዕይ መሳካት እገዛ የሚያደርገውን የአዋላጅ ነርሶች ኮሌጅ ለማቋቋም ከፍተኛ ጥረት ያደረጉ ተጠቃሽ ሰው መሆናቸውንም ዘገባው አስታውሷል፡፡ ፌስቱላ በአፍሪካ ከአስራ ሁለት ሴቶች በአንዷ ላይ የሚከሰት አሳሳቢ የጤና ችግር እንደሆነ መረጃዎች ያመለክታሉ፡፡

Monday, 22 September 2014 14:20

ሃይማኖት አለሙ አረፈ

          ታዋቂው ተዋናይና ዳይሬክተር ረዳት ፕሮፌሰር ሃይማኖት አለሙ፣ ባደረበት ህመም ህክምና ሲከታተል ቆይቶ በትናንትናው ዕለት አረፈ፡፡በአዲስ አበባ ከተማ የተወለደውና በሆለታ ያደገው ሃይማኖት አለሙ፤ የመጀመሪያና የሁለተኛ ደረጃ ትምህርቱን በተፈሪ መኮንን ትምህርት ቤት የተከታተለ ሲሆን፣ በሚኒሶታ ዩኒቨርሲቲ በትወና ጥበብ በከፍተኛ ማዕረግ በመመረቅ የመጀመሪያ ዲግሪውን እንዲሁም በስነጥበባት ሁለተኛ ዲግሪውን ተቀብሏል፡፡ለረጅም አመታት በአሜሪካ የኖረውና በበርካታ ቲያትሮችና ፊልሞች ላይ በተዋናይነት በመስራት የሚታወቀው ሃይማኖት፣ ወደ ኢትዮጵያ ከተመለሰ በኋላ፣ አስታር አድቨርታይዚንግ በተባለው አለም አቀፍ የማስታወቂያና የኮሙኒኬሽን ተቋም ዋና ጸሃፊ ሆኖ ሲሰራ ቆይቷል፡፡ በአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲና በራክማኖቭ ኮሌጅ የትወና ጥበብ ያስተማረው ሃይማኖት፤ በብሔራዊ ትያትር በስራ አስኪያጅነት ያገለገለ ሲሆን በዚሁ ትያትር ቤት በበርካታ ትያትሮች ላይ ተውኗል፡፡ የትወና ብቃቱን ካሳየባቸው ትያትሮች መካከል የታዋቂው ባለቅኔና ፀሐፌ ተውኔት ሎሬት ፀጋዬ ገ/መድህን “እናት ዓለም ጠኑ” እና “ሀሁ በስድስት ወር” ተጠቃሽ ሲሆኑ “ቴዎድሮስ” በተሰኘው ትያትር ላይ በመተወንም ይታወቃል፡፡ ረዳት ፕሮፌሰር ሃይማኖት የሼክሰፒርን “ሃምሌት” የተሰኘ ትያትርም አዘጋጅቷል፡፡

       በዶ/ር አቡሽ አያሌው የተዘጋጁት “አልፋና ኦሜጋ” ቁጥር 2 እና ቁጥር 3 መጽሐፎች ሰሞኑን ለንባብ በቁ፡፡ አዘጋጁ በ“አልፋና ኦሜጋ ቁጥር 1” መጽሐፍ፤ ስለ ሰዎችና ዩኒቨርስ የመጀመሪያና የመጨረሻ ምስጢራት ሰፊ ትንታኔ በመስጠት የጀመሩትን ሃሳብ በቁጥር ሁለትና በቁጥር ሶስት መጽሐፋቸው በስፋት እንዲቃኙት ለማወቅ ተችሏል፡፡ “አልፋና ኦሜጋ” ቁጥር ሁለት፤ ስለ እኛና ስለ ዩኒቨርስ የመጀመሪያና መጨረሻ ምስጢራት አልበርት አንስታይንና ስቴፈን ሐውኪንግ ደርሰውበታል ስለተባለው እውነት፣ ስለ 666 አስገራሚ የዩኒቨርስ ቁጥርነት፣ በድንገት ፈነዳ ስለተባለው መንፈሳዊ እሳት፣ በመንፈሳዊ ሃይል ስለተሞላው ጨለማ፣ በአስገምጋሚው እሳት ውስጥ ተፈጠረ ስለተባለው ሰማይና ምድር እንዲሁም የአልበርት አንስታይንን መሳጭ የህይወት ታሪክ ያካተተ ሲሆን በ125 ብር ለገበያ ቀርቧል፡፡ “አልፋና ኦሜጋ” ቁጥር ሶስት መጽሐፍ ደግሞ በተለይ ከሞት በኋላ ህይወትና የፈጣሪ መኖር በኳንተም ፊዚክስ ስለመረጋገጡ፣ በነፍስ ላይ ስለተካሄዱ ልዩ ልዩ ሳይንሳዊ ጥናቶች፣ የፈጣሪን ህልውና በማያዳግም መልኩ ስላረጋገጡ 15 ትልልቅ ፍልስፍናዎች፣ በፈጣሪ መኖር ስለሚያምኑ የዓለማችን 13 ምርጥ ሳይንቲስቶች እንዲሁም ስለ ገነት፣ ገሃነም፣ መላዕክት፣ ዲያቢሎስና ፈጣሪ፤ ሳይንስ የደረሰበትን እውነታ ያስቃኛል ተብሏል፡፡ በ224 ገፆች የተቀነበበው መፅሃፉ፤ በ100 ብር ለገበያ ቀርቧል፡፡