Administrator

Administrator

       ዛሬ በፖርቱጋል ዋና ከተማ ሊዝበን በሚገኘው  ኢስታድዮ ዳ ሉዝ ስታድዬም ለ59ኛው የአውሮፓ ሻምፒዮንስ ሊግ  ዋንጫ  ሁለቱ የማድሪድ ከተማ ክለቦች ሪያልና አትሌቲኮ ማድሪድ  ይፋጠጣሉ፡፡ በሻምፒዮንስ ሊግ ታሪክ ለፍፃሜ ጨዋታ የአንድ ከተማ ክለቦች ሲገናኙ  ለመጀመርያ ጊዜ  ነው፡፡ የዋንጫ ጨዋታው በ200 አገራት የቀጥታ ቴሌቭዢን ስርጭት ሲኖረው እስከ 1 ቢሊዮን ተመልካች እንደሚያገኝ ተገምቷል፡፡ የአውሮፓ እግር ኳስ ማህበር ዋንጫውን ለሚያሸንፈው ክለብ 10.5 ሚሊዮን ዩሮ እንዲሁም ለሁለተኛው ክለብ ደግሞ 6.5 ሚሊዮን ዩሮ ያበረክታል፡፡ በአጠቃላይ ሁለቱ የማድሪድ ክለቦች እስከ ፍፃሜው በነበራቸው ግስጋሴ ከቴሌቭዥን ስርጭት መብት፤ ከሜዳ ገቢ እና ከተለያዩ ንግዶች በነፍስ ወከፍ እስከ 55 ሚሊዮን ዩሮ ድርሻ ይኖራቸዋል፡፡ በሻምፒዮንስ ሊጉ ከዋንጫው ጨዋታ በፊት በተደረጉት 124 ጨዋታዎች 357 ጎሎች ሲመዘገቡ፤ ኮከብ ግብ አግቢነቱን የሪያል ማድሪዱ ክርስትያኖ ሮናልዶ በ16 ጎሎች እየመራው ነው፡፡
ሁለቱ የማድሪድ ከተማ ክለቦች እርስ በራስ የሚገናኙበት ጨዋታ “ኤል ደርቢ ማድሪሊያኖ” በሚል መጠሪያ ሲታወቅ ከዛሬው የዋንጫ ጨዋታ በፊት  264 ጨዋታዎች ተደርገውበታል፡፡  በ143 ሪያል ማድሪድ ሲያሸንፍ በ64  ጨዋታዎች ያሸነፈው  አትሌቲኮ ማድሪድ ነው፡፡ በ57 ጨዋታዎች ደግሞ አቻ ተለያይተዋል፡፡ ኤልደርቢ ማድሪሊያኖ አንድ ክፍል ዘመን ያስቆጠረ የእግር ኳስ ትንቅንቅ ነው፡፡  ባለፉት አስር ዓመታት ይህን ታላቅ ደርቢ ሪያል ማድሪድና ባርሴሎና የሚገናኙበት ኤልክላሲኮ ሸፍኖት  ቆይቷል፡፡
 የዓለም ሃብታሙ ክለብ ሪያል ማድሪድ ዛሬ ዋንጫውን ካነሳ በውድድሩ ታሪክ ለ10ኛ ጊዜ ይሆናል፡፡ ከዚህ ቀደም 13 ጊዜ ለፍፃሜ ቀርቦ 9 ዋንጫዎችን ወስዷል፡፡ የመጨረሻው ድሉ ከ12 ዓመት በፊት ነው፡፡ በአንፃሩ አትሌቲኮ የሚያገኘው ድል በታሪክ ለመጀመርያ ጊዜ  ነው፡፡ ከ40 ዓመት በፊት ብቸኛውን የፍፃሜ ጨዋታ አድርጎ  በባየር ሙኒክ 5ለ0 ተሸንፎ ዋንጫውን አልምጦታል፡፡ ሪያል ማድሪድ ኮፓ ዴ ላሬይን ቢያሸንፍም የውድድር ዘመኑን ውጤታማ ለማለት የግድ የሻምፒዮንስ ሊግ ዋንጫ ያስፈልገዋል፡፡ ባለፈው ሳምንት   ከ18 ዓመት በኋላ  የላሊጋ ዋንጫን ላገኘው አትሌቲኮ የማድሪድ ከተማ በ200ሺ ደጋፊዎች ተጥለቅልቃ ነበር ፡፡ የአውሮፓን ክብር ደርቦ ካሸነፈ  ደግሞ በከተማዋ የሚኖረው ፌሽታ ሚሊዮኖችን ያሳትፋል ተብሏል፡፡
ሪያል ማድሪድ በአገር ውስጥ ውድድሮች ከ60 በላይ፤ በአውሮፓ ደረጃ ከ11 በላይ ዋንጫዎችን የሰበሰበ ሲሆን አትሌቲኮ  በአገር ውስጥ ውድድሮች 24 በአውሮፓ ደረጃ ደግሞ 5 ዋንጫዎች አሉት፡፡
በስፔን ፕሪሚዬራ ሊጋ ሪያል ማድሪድ  32 ጊዜ ሻምፒዮን ሲሆን አትሌቲኮ ዘንድሮ 10ኛውን የሻምፒዮናነት ክብር አግኝቷል፡፡ በኮፓ ዴላሬይ ሪያል ማድሪድ 19 ዋንጫ ሲወስድ አትሌቲኮ ማድሪድ 10 አለው፡፡ሪያል ማድሪድ ለውድድር ዘመኑ የነበረው በጀት 515 ሚሊዮን ዩሮ ሲሆን በ4 እጥፍ የሚያንሰው የአትሌቲኮ በጀት 120 ሚሊዮን ዩሮ ነው፡፡
ሪያል ማድሪድ ማልያውን ከፍተኛ ስፖንሰርሺፕ ሲያገኝበት አትሌቲኮ ማድሪድ ለ2 የውድድር ዘመን ስፖንሰር አጥቶ የአዘርባጃን መፈክር ላንድ ኦፍ ፋየርን ለጥፎ ቅናሽ ገቢ አለው፡፡
ሪያል ማድሪድ  የተመሰረተው ከ112 ዓመታት በፊት ሲሆን በዘንድሮ አጠቃላይ የተጨዋቾች ስብስቡ በትራንስፈር ማርኬት 505 ሚሊዮን ዩሮ የዋጋ ተመን ሲኖረው  ከተመሰረተ ከ111 ዓመታት የሚሆነው የአትሌቲኮ ማድሪድ የተጨዋቾች ስብስብ ተመኑ 282 ሚሊዮን ዩሮ ነው፡፡

የኢትዮጵያ ሴቶች ብሔራዊ ቡድን (ሉሲዎቹ) በኢኳቶሪያል ጊኒ አስተናጋጅነት በ2007 ዓ.ም. ለሚከናወነው 9ኛው የአፍሪካ ዋንጫ  ለማለፍ  ጥቋቁሮቹን ንግስቶች ከተባሉት የጋና አቻቸው  በደርሶ መልስ ይፋለማሉ፡፡ የመጀመርያው ጨዋታ ነገ በአዲስ አበባ ስታድዬም የሚደረገው ነው፡፡ ሉሲዎቹ በዚሁ ፍልሚያ በሰፊ የግብ ልዩነት ማሸነፍ ከቻሉ የማለፍ እድላቸውን ያጠናክራሉ፡፡ ሁለት የወዳጅነት ጨዋታዎችን ከካሜሮንና ከናሚቢያ ብሔራዊ ቡድኖች ጋር የኢትዮጵያ ሴቶች ብሔራዊ ቡድን በሜዳቸው እና ከሜዳ ውጭ አድርገዋል፡፡ በጥሩ ደረጃ አቋማቸውን በመፈተሽም አስተማማኝ ብቃት ላይ ናቸው፡፡ የኢትዮጵያ ሴቶች ብሄራዊ ቡድን ከፕሪምየር ሊግ 12 ክለቦች የተወጣጡና 16 አዳዲስ ተጨዋቾች በሚገኙበት ቡድን በአጠቃላይ 37 ተጨዋቾች አሰባስቦ ቢያንስ ለወር ያህል ጠንካራ ዝግጅት ሲያደርግ ቆይቷል፡፡

የተራ ሞባይሎች ተፈላጊነት እየቀነሰ፤ “የስማርት ፎን” ሽያጭ ባለፈው አመት አንድ ቢሊዮን ያህል የደረሰ ሲሆን፤ የምርጦች ምርጥ ሆነው የገነኑት የአፕል አይፎን እና የሳምሰንግ ጋላክሲ ሞባይሎች ላይ ፉክክሩ አይሏል - በየገበያው እና በየፍርድ ቤቱ።
አፕል እስካሁን፣ ግማሽ ቢሊዮን አይፎኖችን ሸጧል። ቆየት ብሎ ወደ “ስማርትፎን” ገበያ የገባው ሳምሰንግ፣ ምርቶቹን በፍጥነት በማስፋፋት ከ200 ሚሊዮን በላይ ጋላክሲ ሞባይሎችን ለመሸጥ ችሏል።
አፕል ባለፈው መስከረም ወር ለገበያ ያቀረበው አይፎን 5፤ በመጀመሪያዎቹ ሶስት ቀናት 9 ሚሊዮን ያህል ተሽጦለታል። ከጊዜ ወደ ጊዜ ሽያጩ እየጨመረ፣ ባለፉት አስራ ሁለት ወራት ብቻ፤ 160 ሚሊዮን የተለያዩ የአይፎን ሞባይሎችን ለመሸጥ ችሏል። ነገር ግን፤ የሳምሰንግ ጋላክሲ ብርቱ ተፎካካሪ ሆነውበታል።
ከአይፎን በሶስት አመት ዘግይቶ የመጣው የሳምሰንግ ጋላክሲ፤ በፍጥነት እየተሻሻለ ከጋላክሲ ኤስ1 ዘንድሮ ጋላክሲ ኤስ5 ደርሷል። ባለፈው ወር  ለገበያ የቀረበው ጋላክሲ ኤስ5፤ ከአይፎን 5 ያልተናነሰ ገዢ እያገኘ እንደሆነ ተዘግቧል።



በሃይማኖት አክራሪነቱ ምክንያት ተቃውሞ የገጠመውን “የሙስሊም ብራዘርሁድ መንግስት” በመገልበጥ ስልጣን የያዙት ጄ/ል አልሲሲ፣ በግብፅ ፕሬዚዳንታዊ ምርጫ ያለ ብዙ ፉክክር በሰፊ ልዩነት ያሸንፋሉ ተብሏል።
በእርግጥ ምርጫው የሚጀመረው  ሰኞ ነው። ነገር ግን፤ በውጭ የሚኖሩ ግብፃዊያን ከወዲሁ ድምፅ ሰጥተው ቆጠራ ተካሂዷል። በዚሁ ቆጠራ፤ ጄ/ል አልሲሲ፣ 94.5% ድምፅ ሲያገኙ፣ ወደ ሶሻሊዝም የሚያዘነብሉ ተቀናቃኛቸው 5.5% ድምፅ ማግኘታቸውን ዎልስትሪት ጆርናል ዘግቧል።
ሰኞ በሚጀመረው የአገር ውስጥ ምርጫም አልሲሲ አብዛኛውን ድምፅ እንደሚያገኙ ከመራጮች የተሰበሰበሰ አስተያየት ይጠቁማል። በእርግጥ፤ በጭራሽ ድምፅ ላለመስጠትና ላለመምረጥ የወሰኑ ግብፃዊያን ብዙ ናቸው። ከፊሎቹ ጄነራሉን በጠላትነት የሚቃወሙ የሙስሊም ብራዘርሁድ ደጋፊዎች ናቸው። ከፊሎቹ ደግሞ፤ የተሻለ አማራጭ የያዘ ደህና ፓርቲና ደህና ፖለቲከኛ በማጣት ከምርጫው ራሳቸውን አግልለዋል። ከእነዚህ ውጭ የሆነው አብዛኛው ግብፃዊ መራጭ፤ ለጊዜው ለአገሪቱ የሚበጃት ጄነራል አልሲሲን የመሰለ ጨከን ያለ መሪ ነው ብለው ያምናሉ።
በሌላ በኩል፤ በመፈንቅለ መንግስት ስልጣን ይዘው ከሰላሳ አመት በላይ ግብፅን የገዟት ሆስኒ ሙባረክ፣ 3 ሚሊዮን ዶላር ገደማ የመንግስት ገንዘብ አጭበርብረዋል በሚል ሰሞኑን የሶስት አመት እስር ተፈርዶባቸዋል። ልጃቸው ደግሞ የአራት አመት እስር። ከዚሁም ጋር የ14 ሚሊዮን ዶላር ቅጣት ተወስኖባቸዋል።

         ጡረተኛው ጄነራል ካሊፋ ሂፍጠር ከሁለት ወር በፊት አስቀድመው ተናግረዋል። “የሊቢያ መንግስት የሃይማኖት አክራሪዎችንና አሸባሪዎችን መቆጣጠር ካልቻለ፤ የራሴን እርምጃ እወስዳለሁ” በማለት በይፋ የተናገሩት በየካቲት ወር ነው። አንዳንድ ሊቢያውያን፤ “ምነው እንደአፋቸው ባደረጉት!” በማለት ተመኝተዋል። አንዳንዶች ደግሞ፤ “ጦር ሰራዊት የሌለው የጦር ጄነራል!” በማለት ተሳልቀዋል። ከአርባ አመት በላይ ሊቢያን አንቀጥቅጠው የገዟት ሶሻሊስቱ ሙዐመር ጋዳፊ በአመፅ ከስልጣን ወርደው ከተገደሉ በኋላ ለጥቂት ወራት የተስፋ ጭላንጭል ቢታይም፤ ብዙም ሳይቆይ አገሪቱ ወደ ግጭትና ትርምስ ተንሸራትታለች።
ፓርላማው፤ በአክራሪዎች እና አክራሪነትን በሚቃወሙ በርካታ ፓርቲዎች ለሁለት ተከፍሏል። አክራሪዎቹ እርስበርስ ይቀናቀናሉ - በጭካኔ ብዛት ይፎካከራሉ። አክራሪነትን የሚቃወሙት ፓርቲዎችም ቢሆኑ፤ በጎሳ እየተቧደኑ ይሻኮታሉ። ፉክክሩና ሽኩቻው፣ በንግግርና በፅሁፍ ብቻ አይደለም። ዘ ጋርድያን እንደዘገበው፤ እያንዳንዱ ፓርቲና ቡድን፤ የየራሱ ጦርና ታጣቂ ቡድን አለው። አንዳንዶቹ በታንክና በከባድ መሳሪያ የተደራጁ፤ በሺ የሚቆጠሩ ታጣቂዎችን ያሰለፉ ናቸው። የታጣቂ ቡድኖቹ ብዛት በመቶ ይቆጠራል። በሊቢያ የጦር መሳሪያ እጥረት የለም። አንዳንዶቹ  እንደአቅሚቲ በወረዳ፣ ከዚያም አልፎ በመንደርና በሰፈር ግዛታቸውን ለማስፋፋት የታጣቂ ቡድን ያንቀሳቅሳሉ። ገሚሶቹ ግን ወደቦችንና የነዳጅ ማውጫ ቦታዎችን ለመቆጣጠር ይዘምታሉ። ሌት ተቀን፣ ግድያ፣ ተኩስ፣ ፍንዳታ፣ ውጊያ ነው። የሊቢያ የነዳጅ ምርት፣ በቀን 1.4 ሚሊዮን በርሜል እንደነበረ የገለፀው ዎልስትሪት ጆርናል፤ አሁን በታጣቂዎች ግጭት የተነሳ የአገሪቱ የነዳጅ ምርት ወደ 200ሺ እንደወረደ ዘግቧል።
ባለፈው የካቲት ወር በትሪፖሊ በርካታ ነዋሪዎች በታጣቂዎች ከተገደሉ በኋላ ከፍተኛ ተቃውሞ በመነሳቱ፤ ዋና ከተማዋን ተቀራምተው የነበሩ ታጣቂ ቡድኖች ከተማዋን ለቀው እንዲወጡ ተደርገዋል። ግን ብዙም አልራቁም። ዙሪያውን በተለያዩ ከተሞች ካምፕ ሰርተው ተከማችተዋል። ትሪፖሊ የተወሰነ እፎይታ ብታገኝም፤ እንደ ቤንጋዚና ሚዝራታ የመሳሰሉ ከተሞች ግን የታጣቂ ቡድኖች መፈንጫ ሆነዋል። በየሳምንቱ፤ በደርዘን የሚቆጠሩ ፖሊሶች፣ ምልምል ወታደሮችና ዳኞች በተለያዩ ታጣቂ ቡድኖች ይገደላሉ - በተለይ ደግሞ ከአልቃይዳ በማይተናነሱ አክራሪ ቡድኖች። አነስተኛ ከተሞችና የገጠር መንደሮች ደግሞ፣ በጎሳ በተቧደኑ ታጣቂዎች ይታመሳሉ።
በጎሰኝነት እና በሃይማኖት አክራሪነት የተቃወሱ አገሮች ውስጥ፤ እንደ ሞሶሎኒና ሂትለር፤ ወይም እንደ ግብፁ ጄነራል አልሲሲ፤ “እናት አገር” ወይም “አባት አገር” የሚል መፈክር ይዞ የሚመጣ ብሔረተኛ መች ይጠፋል? በሊቢያ ደግሞ ጄነራል ካሊፋ ሂፍጠር።
ከአርባ አመት በፊት የጋዳፊ ወዳጅ የነበሩት ጄ/ል ሂፍጠር፤ ጎረቤት አገር ላይ የወረራ ዘመቻ እንዲመሩ ተመድበው ስላልተሳካላቸው ነው የጋዳፊ ጥርስ ውስጥ የገቡት። እንደምንም አምልጠው በስደት ወደ አሜሪካ የገቡት ጄ/ል ሂፍጠር፤ ተቃዋሚዎችን ለማደራጀት ለበርካታ አመታት ቢጣጣሩም የጋዳፊን መንግስት ሊያነቃንቁት አልቻሉም። የዛሬ 3 አመት በአረብ አገራት ሰፊ የተቃውሞ አመፅ የተቀሰቀሰ ጊዜ ነው፤ ወደ ሊቢያ ተመልሰው የወታደራዊ አመፅ መሪ የሆኑት። ከድል በኋላ የመከላከያ ሃይል ዋና አዛዥ የመሆን እድል አላገኙም። ምክትል ዋና አዛዥ ሆነው ትንሽ ከቆዩ በኋላ፤ ያንኑም ትተው የወጡት ጄ/ል ሂፍጠር፤ ለሁለት አመታት ያህል ድምፃቸው አልተሰማም። ድምፃቸውን ሊያሰሙ ቢሞክሩም፤ ያን ያህልም ሰሚ አልነበራቸው። ከጊዜ ወደ ጊዜ በጎሳ የተቧደኑ ታጣቂዎች እና በተለይም የሃይማኖት አክራሪ ቡድኖች የሚፈፅሙት ግድያ፣ ግጭትና ፍንዳታ እየተባባሰ፣ በሰላም ወጥቶ መመለስ እየጠፋ ሲመጣ አብዛኛው ሊቢያዊም ሲማረር ግን ሰሚ ተገኘ።
ለጄነራሉ ጆሯቸውን ለመስጠት ቀዳሚ ከሆኑት መካከል፣ ፖሊሶችና ወታደሮች ናቸው። የታጣቂ ቡድኖች የግድያ ዘመቻ፤ በፖሊሶችና ወታደሮች ላይ ይበረታልና። በጎሳ የተቧደኑ አንዳንድ ታጣቂዎችንም ለማግባባት ሞክረዋል ጄ/ል ሂፍጠር። እንዲህ አይነት ዝግጅቶችን ለሁለት ወራት እንዳካሄዱ የሚገልፁት ጄ/ል ሂፍጠር፤ ባለፈው ሳምንት በቤንጋዚና በትሪፖሊ ከተሞች ወታደሮችን በማሰማራት ወደ ጥቃት ዘመቻ እንደተሸጋገሩ አውጀዋል። ያሰባሰቡትን ወታደራዊ ሃይል፤ “የሊቢያ ብሔራዊ ጦር” ሲሉ ሰይመውታል። “አባት አገር ተደፍሯል” የሚሉት ጄ/ል ሂፍጠር፤ የዘመቻው መጠሪያ ስም፤ “የሊቢያን ክብር የማስመለስ ዘመቻ” የሚል እንደሆነ ተናግረዋል። ቤንጋዚ ከተማ ውስጥ፤ ባለፈው አርብ ሶስት አክራሪ ቡድኖች ላይ ጥቃት ከፈፀሙ በኋላ፤ እሁድ እለት በትሪፖሊ ፓርላማ ላይ ታጣቂዎችን አዝምተዋል።
የፓርላማው የስልጣን ዘመን ካበቃ ሁለት ወር ስላለፈው ህጋዊ ስልጣን የለውም የሚሉት ጄ/ል ሂፍጠር፤ “አክራሪዎች ፓርላማውን ተቆጣጥረውታል፤ ጠቅላይ ሚኒስትሩ የአክራሪ ቡድን ተወካይ ናቸው፤ ብሔራዊ ጦርና ብሔራዊ ፖሊስን ከማደራጀት ይልቅ አክራሪ ታጣቂ ቡድኖችን በመደገፍ ያጠናክራሉ” በማለት ፓርላማ ላይ የፈፀሙት ጥቃት ተገቢ እንደሆነ ይናገራሉ። አክራሪ ቡድኖችና ታጣቂዎች በድርድርና በውይይት አያምኑም፤ ስለዚህ እስክናጠፋቸው ድረስ እንዋጋለን ብለዋል ጄነራሉ።
የጄነራሉን ድርጊት ለማውገዝ እንደማይፈልጉ የገለፁ አንዳንድ ሚኒስትሮችና የፓርላማ አባላት፤ አክራሪ ቡድኖችን መቃወም ተገቢ ነው ብለዋል። የተወሰኑ ሚኒስትሮች ደግሞ፤ የጄነራሉ ጥቃት አደገኛ ነው፤ በቋፍ ያለችውን አገር ወደ ለየለት ጦርነት ሊያስገባት ይችላል ብለዋል። ጠቅላይ ሚኒስትሩና በርካታ ባለስልጣናት ግን፤ የጄነራሉ ዘመቻ ከመፈንቅለ መንግስት ተለይቶ አይታይም ሲሉ አስጠንቅቀዋል። በትሪፖሊ ዙሪያ የሰፈሩ ታጣቂ ቡድኖች ወደ ዋና ከተማዋ በመግባት የጄነራሉን ጥቃት እንዲከላከሉ ጥሪ ያስተላለፉት ጠቅላይ ሚኒስትር፤ የቤንጋዚ አየር ማረፊያ አገልግሎት እንዳይሰጥ ትዕዛዝ አስተላልፈዋል። የአገሪቱ መከላከያ ሃይል፤ በጡረተኛው ጄነራል ላይ እርምጃ እንዲወስድም በይፋ አዘዋል - ጠቅላይ ሚኒስትሩ። ነገር ግን ትዕዛዛቸው አልሰራም። በሁለት ከተሞች የሚገኙ የአየር ሃይል ካምፖች በጡረተኛው ጄነራል ስር ለመመራት በመወሰናቸው፤ ሄሌኮፕተሮችና የጦር አውሮፕላኖች በቤንጋዚ ዘመቻ ላይ ተካፍለዋል። የመከላከያ ሃይል ወታደራዊ ፖሊስ አዛዥ በበኩላቸው፤ በጄነራል ሂፍጠር መሪነት የአገሪቱ መንግስት ከስልጣን መታገዱን በማወጅ፤ ጊዜያዊ መንግስት እንደሚመሰረት ገልፀዋል።
ለሁለት አመት ተረስተው የነበሩት ጡረተኛ ጄነራል፤ አሁን ወታደራዊ ልብስ ከነማዕረጋቸው ለብሰው በሳምንት ውስጥ ገናና ለመሆን ቢችሉም፤ የመንግስት ስልጣን ለመቆጣጠር አቅም ይኑራቸው አይኑራቸው ገና አልታወቀም። ለእርስ በርስ ጦርነት የሚሆን አቅም እንዳላቸው ግን አያጠራጥርም። ለዚህም ይመስላል፤ የአልጄሪያ መንግስት ልዩ ወታደራዊ ሃይል በመላክ ዲፕሎማቶቹንና ዜጎቹን ከሊቢያ ሲያስወጣ የሰነበተው። የሞሮኮ መንግስትም አምስት ሺ ወታደሮችን ወደ ድንበር አሰማርቷል። የአውሮፓ አገራትና አሜሪካ፤ ዜጎቻቸውን በአፋጣኝ ለማስወጣት መጣደፍ ጀምረዋል። በአጠቃላይ በግጭት የምትታመሰው ሊቢያ፤ አሁን እንደገና መጨረሻው በማይታወቅ የጦርነት ውጥረት ውስጥ ገብታለች።

የፕሬዚዳንት ሙሴቪኒን መንግስት ለመጣል ከበርካታ አመታት የተዋጉት ጆሴፍ ኮኒ፤ ልጃቸውን የወለዱትና ያሳደጉት እዚያው በረሃ ውስጥ ነው። ግን በአባቱ ስም አይደለም የሚጠራው። ሳሊም ሳልህ ይባላል።
ኤፍፒ እንደዘገበው፤ጆሴፍ ኮኒ ልጃቸውን ሳሊም ሳልህ ብለው የሰየሙት፣ ከፕ/ት ሙሴቪኒ ወንድም ጋር ሞክሼ እንዲሆን ስለፈለጉ ነው። ራሳቸውን እንደ ፕሬዚዳንት ልጃቸውን ደግሞ እንደ ተተኪ ፕሬዚዳንት ማየታቸው ሊሆን ይችላል። በረሃ ተወልዶ በረሃ ያደገው ልጅ፤ ዛሬ የ22 አመት ጎረምሳ ሆኗል። ሰሞኑን ደግሞ የአማፂው ቡድን ምክትል መሪ እንዲሆን በአባቱ ሹመት ተሰጥቶታል።
የክርስትና አክራሪነት ላይ የተመሰረተውና “ሎርድስ ሬዚስታንስ አርሚ” የተሰኘው አማፂ ቡድን በዩጋንዳ፤ ብዙ ሺዎችን በጭካኔ ከመጨፍጨፉም በተጨማሪ ከ60ሺ በላይ ሕፃናትን ጠልፎ ለውጊያ በማሰማራትና ለወሲብ በማስገደድ ይታወቃል። በፈጣሪ የተመረጥኩ ነብይ ነኝ የሚሉት ጆሴፍ ኮኒ፤ አላማዬ ሃይማኖታዊ መንግስት ለመመስረት ነው ይላሉ።

ታይላንድ የገዢ ፓርቲ ባለስልጣናትና ተቃዋሚዎች ሐሙስ እለት ታስረዋል

ገዢውን ፓርቲ የሚደግፉና የሚቃወሙ ቡድኖች በሚያካሂዱት አመፅ ስትታመስ የከረመችው ታይላንድ፤ በዚህ ሳምንት ለወታደራዊ መፈንቅለ መንግስት ተዳርጋለች። “የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ” ተግባራዊ ለማድረግ መወሰኑን ማክሰኞ እለት የገለፀው የአገሪቱ የጦር ሃይል፣ ውሳኔው የመንግስት ግልበጣ አይደለም በማለት ደጋግሞ ተናግሯል። “የጦር ሃይል፣ የመንግስት ግልበጣ ሳያካሂድ በአገሪቱ ላይ የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ የመጫን ስልጣን አለው” ሲልም ከመቶ አመት በላይ ያስቆጠረና የተረሳ ጥንታዊ የሕግ አንቀፅ በመጥቀስ ለማስረዳትና ለማስተባበል ሞክሯል። ማስተባበያው ግን ከሁለት ቀን በላይ አልዘለለም። ሐሙስ እለት፤ ወደለየለት መፈንቅለ መንግስት ተሸጋግሯል።
ስልጣን የተቆጣጠረው የጦር ሃይል፤ የተቃውሞ ሰልፎችን በማገድ ወታደሮችን ለቁጥጥር ካሰማራ በኋላ የዋና ከተማዋ ጎዳናዎች ፀጥ ረጭ ብለዋል። ከተቀናቃኝ ፓርቲዎች ጋር ጎራ ለይተው ቀውሱን ያባብሳሉ የተባሉ 14 የቴሌቪዥን ቻናሎችና 3000 የሬዲዮ ቻናሎችም ለጊዜው ታግዳችኋል ተብለዋል።
ከዚሁ ጎን ለጎን፤ ተቀናቃኝ ፓርቲዎች እንዲሁም ከፓርቲዎቹ ጋር ጎራ ለይተው የተሰለፉ ተቀናቃኝ ቡድኖች ለውይይት እንዲሰበሰቡ ወታደራዊው ሃይል ማክሰኞ እለት በቴሌቪዥን ማሳሰቢያ አሰራጭቷል። ለአመታት ሲወዛገቡ የቆዩትና በተለይም ባለፉት ስድስት ወራት በየአደባባዩ ሲጋጩ የከረሙት ተቀናቃኝ ፓርቲዎችና ቡድኖች፤ አንድም ጊዜ ተቀራርበው ለመነጋገር ፈቃደኛ አልነበሩም።
ወታደራዊው ሃይል ማሳሰቢያ ባሰራጨ ማግስት ግን፣ ለውይይት ፈቃደኛ ሆነው ተሰብስበዋል። ሁለት ሰዓት ተኩል በፈጀው ውይይት አንዳች የመፍትሄ ሃሳብ ላይ ባይደርሱም ጥሩ ጅምር ነው ብሏል የወታደራዊው ሃይል ቃል አቀባይ። ፓርቲዎቹ እንደገና ሃሙስ እለት ለመገናኘት ተቀጣጥረው ነበር - በስልጣን ክፍፍልና በምርጫ ዝግጅት ላይ ለመወያየት።
የሃሙሱ ስብሰባ የተካሄደው በጦር ሃይሎች ክለብ ውስጥ ነው። ምርጫ እስኪካሄድ ድረስ በጊዜያዊነት ስልጣን የያዘው ገዢ ፓርቲና ተቃዋሚ ፓርቲ፤ እንዲሁም ጎራ ለይተው ከሁለቱ ፓርቲዎች ጋር የተሰለፉ ተቀናቃኝ ቡድኖች ለስብሰባው መጥተዋል። ሚኒስትሮች፣ የፖለቲካ ፓርቲ መሪዎች፣ የፖለቲካ ቡድኖ ተወካዮች፤ ማክሰኞ እለት እንዳደረጉት ሃሙስ እለትም ወደ ሁለት ሰዓት ገደማ ተነጋግረዋል። ግን፤ ሊስማሙ አልቻሉም። ገዢው ፓርቲ ስልጣን ለመልቀቅ ፈቃደኛ አይደለም። ተቃዋሚው ፓርቲ ስልጣን ካልተሰጠኝ ሞቼ እገኛለሁ ይላል።  ይሄኔ ነው፤ የጦር ሃይሎች ዋና አዛዥ ጄነራል ፕራዩዝ ቻንኦቻ፤ ትእግስታቸው እንዳለቀ የገለፁት። ተሰብሳቢዎቹም ሆኑ ውይይቱን ለመዘገብ የመጡ ጋዜጠኞች ምን እየተፈጠረ እንደሆነ አላወቁም። “የናንተ ንግግር ማለቂያ የለውም” ሲሉ የተናገሩት ጄ/ል ፕራዩዝ፤ “ከአሁን ጀምሮ፣ ስልጣን በኔ እጅ ውስጥ ገብቷል” በማለት ነገሩን በአጭሩ ቋጩት። ለውይይት የተሰባሰቡት ሚኒስትሮች፣ ተቃዋሚዎች፣ የፖለቲካ ቡድን መሪዎች በዚሁ የሚሰነባበቱ መስሏቸው ነበር። ነገር ግን እዚያው እንደተሰበሰቡ ወደ ምድር ጦር ካምፕ ተወስደው እንዲታሰሩ ነው ጄነራሉ ትዕዛዝ የሰጡት። ፖለቲከኞች ሲወያዩ ለማየት የሄዱ ጋዜጠኞች፣ ፖለቲከኞች ሲታሰሩ አይተው ተመለሱ። በስብሰባው ላይ ያልተገኙ ሚኒስትሮችና የተቃዋሚ ፓርቲ መሪዎች፣ በአንድ ቀን ውስጥ እጃቸውን እንዲሰጡ በሚዲያ ማስጠንቀቂያ ተሰራጭቷል።
የጦር ሃይል ዋና አዛዥ ጄ/ል ፕራዩዝና ምክትላቸው፤ እንዲሁም ኤታማዦር ሹም፣ የባህር ሃይል፣ የአየር ሃይልና የፖሊስ ዋና አዛዦችን ያካተተ የአምስት ጄነራሎች ኮሚቴ፤ የመንግስትን ስልጣን እንደተቆጣጠረ ጄ/ል ፕራዩዝ ገልፀዋል። ትምህርት ቤቶች ተዘግተዋል። ሁሉም የሚዲያ ተቋማት፤ የግል የቴሌቪዢንና የሬድዮ ጣቢያዎችም ጭምር፤ ከወታደራዊው ጁንታ ከሚመጣላቸው ነገር ውጭ ምንም እንዳያሰራጩ ማስጠንቀቂያ ተሰጥቷቸዋል። የፖለቲካ ፓርቲ እንቅስቃሴ፣ ሰላማዊ ሰልፍና ስብሰባ ተከልክሏል። የማታ ሰዓት እላፊ ታውጇል።
በአጠቃላይ፤ ከመፈንቅለ መንግስት ጋር ተያይዘው የሚመጡ እርምጃዎች በሙሉ በፍጥነት ተከናውነዋል። ፍጥነታቸው አይገርምም። ታይላንድ በመፈንቅለ መንግስት በኩል፤ ከፍተኛ ልምድ የተከማቸባት አገር ናት። በመቶ አመታት ውስጥ 19 የመፈንቅለ መንግስት ታሪኮችን በማስተናገድር በአለም ቀዳሚ አገር ናት ተብሎላታል።

Saturday, 24 May 2014 15:13

የሳምንቱ ምርጥ 10

Billboard TOP 10 Albums

Turn Blue  -The Black Keys
Xscape   -Michael Jackson
NOW 50   -Various Artists
Frozen   -Soundtrack
Rewind   -Rascal Flatts
Blue Smoke   -Dolly Parton
Unrepentant Geraldines   -Tori Amos
Shine On  - Sarah McLachlan
Storyline   -Hunter Hayes
Sovereign   -Michael W. Smith




Top 10 Best Sellers  Books on Amazon
1.The Fault in Our Stars by John Green
Oh, The Places You’ll Go! by Dr. Seuss
The Conscious Parent by Dr. Shefali Tsabary
Capital in the Twenty-First Century by Thomas Piketty
One Nation by Ben Carson M.D.
Frozen Little Golden Book by Victoria Saxon
.City of Heavenly Fire by Cassandra Clare
Ultimate Sticker Book: Frozen by DK Publishing
The Goldfinch: A Novel by Donna Tartt
 Skin Game (Dresden Files) by Jim Butcher


Box Office Top 10

Godzilla
Neighbors
The Amazing Spider-Man 2
Million Dollar Arm
The Other Woman
Heaven is for Real
Rio 2
Captain America: The Winter Soldier
Legends of Oz: Dorothy’s Return
Mom’s Night Out

Saturday, 24 May 2014 15:13

የግጥም ጥግ

የዕድገት 10ቱ ቃላት!
አንዱ የዕድገት ትርጉሙ ጠፍቶበታል
አንዳንዱ ቁልቁል ማደግም ዕድገት ነው ይላል!
አንዳንዱ እንኳን ማደግ ከነመወለዱም ጠፍቶበታል!
አንዳንዱ እንዴት እንደሚታደግ ማወቅ ተስኖታል!
አንዳንዱ ፎቅ ይሰራ ይሰራና የሚከራይ ሲያጣ፤ “ይህ ህዝብ ዕድገት አይገባውም” ይላል፡፡
አንዳንዱ ፎቅ ሰርቶ ሰርቶ ሰርቶ ጫፍ ይወጣና “መሬት ማለት ምን ማለት ነው?” ብሎ ይጠይቃል፡፡
አንዳንዱ “ዕድገት አለ ግን ወረቀት ላይ ነው ያለው፡፡ ስለዚህ ዋናው የወረቀት ዋጋ ማደግ ነው” ይላል፡፡
“አንዳንዱ ዕድገት ማለት ሌሎች ሲያድጉ ማየት ነው፡፡ ስለዚህ የድንኳን ሰባሪ እድገት ነው”! ይላል
አንዳንዱ እድገት ማለት ከዚህ ወዲያም ለምን እንዳላደግን ማሰብ ነው፡፡ በቃ ካሰብክ የግድህን ታድጋለህ” ይላል፡፡
አንዳንዱ ግን ጥብስቅ አድርጎ… አድጎ… አድጎ ከአቅሙ በላይ ተመንድጎ ማደጉን ማቆሙ ጨንቆት “ብቻዬን አድጌ እስከመቼ! የሚያግዘኝ ይቅር የሚቃወመኝ እንዴት ይጥፋ?
የኔን ፎቅ ማየት ካልቻለ
ጎጆው ሲፈረስ ይማር የለ?”
በቃ ዛሬ ገና ይግባው
ቦታ ቀይሮ ሲሰፍር ለውጥም ዕድገትም የሱው ነው፡፡
ግንቦት 2006 ዓ.ም (ለአፍቃሬ ዕድገቶች)

ወ/ሮ ይድነቃቸው የሁለት ልጆች እናት ናት፡፡ ልጆቿ በመጽሐፍ ቅዱስ ዕውቀት ተኮትኩተው እንዲያድጉ ስለፈለገች፣ የመጽሐፍ ቅዱስ ዕውቀትን በቀላል አቀራረብና ቋንቋ የያዙ የልጆች መፃሕፍት ፍለጋ ብዙ ቦታዎች ጠይቃ ማጣቷን ትናገራለች፡፡ የዚህች እናት ገጠመኝ በአገራችን ያለውን የመፃሕፍት ስርጭት ችግር ያመለክት እንደሆነ እንጂ ለሕፃናት የተዘጋጁ መፃሕፍት የሉም ወደሚል ድምዳሜ አያደርሰንም፡፡
የመፃህፍቱን ሥርጭት እንዲሁም ብዛትና ዓይነቱን ለማወቅ የሚቻልበት መንገድ የለም እንጂ ለሕፃናት የታለሙ በርካታ መፃሕፍት ተጽፈዋል፡፡ የደራሲ ማይክል ዳንኤል አምባቸው ሙት ዓመት በጣይቱ ሆቴል ሲከበር እንደተገለፀው፤ ሟቹ አብዛኛው በእንግሊዝኛ ቋንቋ ቢሆንም  40 የልጆች መፃሕፍትን አዘጋጅተው አሳትመዋል፡፡
በሌላ አጋጣሚ ደግሞ 49 የልጆች መፃሕፍት አሳትመዋል የተባሉ አንድ ደራሲ የማግኘት እድል ገጥሞኝ ነበር፡፡ የፃፏቸውን 49 የልጆች መፃሕፍት፣ በየክልሉ ባሉ ትምህርት ቤቶች ማከፋፈላቸውን ነግረውኛል፡፡
ለልጆች ታስበው የታተሙት መፃሕፍት ቁጥር ቀላል አይደለም፤ ይዘትና አቀራረባቸው ግን ብዙ ሊያነጋግር እንደሚችል እሙን ነው፡፡ በቅርቡ “የሉሲ ክዋክብትና ሌሎችም” በሚል ርዕስ በደራሲ ገብረክርስቶስ ኃይለሥላሴ የተዘጋጀው የልጆች መፅሃፍ፤ ልጆች መልካም ሥነ ምግባር እንዲማሩበት ታስቦ የተሰናዳ ሲሆን ለልጆች የሚዘጋጁ መፃሕፍት እንዴት መቅረብ እንዳለባቸው ጥሩ ማሳያ ይመስለኛል፡፡
በ145 ገፆች ተቀንብቦ የቀረበው መጽሐፉ፤ በአራት ምዕራፎች 36 ተረቶችን ይዟል፡፡ “ከአሁን ቀደም ከጓደኛዬ ጋር ‹ናብሊስ› በሚል ርዕስ ከ5ኛ እስከ 8ኛ ክፍል ላሉ ተማሪዎች ሊሆን የሚችል የልጆች መጽሐፍ አዘጋጅቻለሁ” ሲሉ በመግቢያው ላይ ያሰፈሩት ደራሲው “ይህ ጥረት በተመሳሳይ ሁኔታ መቀጠል እንዳለበት አጥብቄ ስላመንሁበት፣ ከ1ኛ እስከ 5ኛ ክፍል ለሚማሩ ተማሪዎች የሚሆን ተነባቢና ጣፋጭ ታሪኮችን በውርስ ትርጉም መልክ አዘጋጅቼ አቅርቤያለሁ” ብለዋል፡፡ ታሪኮቹ በ24 ስዕሎች ታጅበው ነው የቀረቡት፡፡
ደራሲ ገብረክርስቶስ፤ ለሕፃናት የሚዘጋጁ መፃሕፍትን በዕድሜና በክፍል ደረጃቸው እየለዩ ማቅረብ እንደሚገባ አስምረውበታል፡፡ ርዕሰ ጉዳዩ ምንም ይሁን ለአዋቂዎች እንዴት መቅረብ እንደሚችል፣ ለልጆችስ በምን መልኩ እንደሚዘጋጅ በደራሲው መፅሐፍ በተመሳሳይ ጭብጥ ከቀረብ ታሪክ ጋር ለማመልከት እሞክራለሁ፡፡
በ“ሉሲ ክዋክብትና ሌሎችም” መጽሐፍ ውስጥ ስለ ስስትና አልጠግብ ባይነት የቀረበው ታሪክ “ቀላዋጩ ሸረሪት” የሚል ርዕስ አለው፡፡ በድሮ ዘመን ሸረሪት ወገቡ ወፍራም ነበር፡፡ በአንዱ ዕለት ጫካ ውስጥ ያሉ ሁለት እንስሳት፣ በሁለት የተለያዩ መንደሮች ድግስ መሰናዳቱን ነገሩት፡፡ በሁለቱም ድግስ መብላት የፈለገው ሸረሪት፣ የትኛው ድግስ ቀድሞ እንደሚጀመር ስላላወቀ፣ ዘዴ ማፈላለግ ያዘ፡፡
“ወደ ቤቱ እየከነፈ ሄደና ረጃጅም ገመዶችን ያዘ፡፡ ሁለቱን ወንድና ሴት ልጆቹንም ጠራቸው፡፡ ልጆቹንና ገመዶቹን ይዞ ላይ ሰፈርንና ታች ሰፈርን በአማካይ ወደሚያዋስነው ወንዝ ሄዱ፡፡ አቶ ሸረሪት፤ በአንዱ የገመድ ጫፍ ወገቡን አሰረና ሌላኛውን ጫፍ ለሴት ልጁ ሰጣት፡፡ እርሷም የገመዱን ጫፍ እየጎተተች ወደ ታች ሰፈር ሄዳ፣ ግብዣው ሲጀመር ገመዱን በመሳብ ምልክት እንድትሰጠው ታዘዘች፡፡ በሁለተኛውም ገመድ በተመሳሳይ ወገቡን አስሮ፣ ጫፉን ለወንድ ልጁ ሰጠው፡፡ ወንድ ልጁም ወደ ላይኛው ሰፈር ሄዶ እንዲያመለክተው ታዘዘ፡፡ ሁለቱም ልጆቹ የታዘዙትን ለመፈፀም ወደየተመደቡበት ቦታ ገመድ እየጎተቱ ሄዱ፡፡ አቶ ሸረሪት ወገቡን በሁለት ገመዶች እንደታሰረ በመሀል ሆኖ ይጠባበቅ ጀመር…
“አጋጣሚ ሆኖ የሸረሪት ሀሳብ እንዳቀደው አልሆነም፡፡ የላይ ሰፈርና የታች ሰፈር የግብዣው ሰዓት ተመሳሳይ ሆነ፡፡ ሁለቱ የሸረሪት ልጆች፣ ግብዣዎቹ እንደተጀመሩ አባታቸው እንዳዘዛቸው ለመፈጸም ገመዶቻቸውን መሳብ ጀመሩ፡፡ ምስኪኑ አባት፤ ሸረሪት በሁለት አቅጣጫ በሚሳቡ ገመዶች ተወጥሮ በመሀል ተንጠለጠለ፡፡”
“ሸረሪት ወገቡ ቀጥኖ የሚታየው በዚህ ምክንያት ነው የሚለው ይህ ታሪክ በመቋጫ ላይ ልጆች አልጠግብ ባይና ስስታም እንዳይሆኑ የሚያስተምር ሀሳብ አቅርቧል፡፡
“በዓለም የታወቁ አጫጭር ልቦለዶች” በሚል ርዕስ በአምሳሉ አክሊሉ ተተርጉሞ፣ በ1981 ዓ.ም ለአንባብያን የቀረበው መጽሐፍም ስስትና አልጠግብ ባይነት ምን ጉዳት እንደሚያስከትል የሚያስተምር ታሪክ ይዟል፡፡ ከሩስያዊው ደራሲ ሊዎ ቶልስቶይ ሥራዎች ተወስዶ “ላንድ ሰው ምን ያህል መሬት ይበቃዋል?” በሚል ርዕስ በቀረበው ልቦለድ ውስጥ፣ አንድ ደሀና ምንም ያልነበረው ገበሬ፣ ሀብት ማካበትን ዓላማው አድርጎ መንቀሳቀስ ሲጀምር፣ የስግብግብና አልጠግብ ባይነት ስሜቱ አጉል አወዳደቅ ላይ እንደጣለው ያስቃኛል፡፡
የልቦለዱ ገፀ ባሕሪ ሚስት፣ ልጆች፣ ከሲታም ቢሆኑ የቤት እንስሳት፣ አነስተኛም ቢሆን የራሱ መሬትና ኑሮ ነበረው፡፡ ይህንን ኑሮውን ሌሎች ሲተቹበት ነበር ሀብት ለማፍራት መንቀሳቀስ የጀመረው፡፡ በምኞት፣ በጥረትና በድካም ከቦታ ቦታ እየተንቀሳቀሰ በርካታ መሬትና ሀብት አፈራ፡፡ ከእርካታ ጋር መገናኘት ግን ሳይቻለው ስለቀረ፣ የተጨማሪ መሬት ባለቤት ለመሆን ጉጉትና ፍላጎቱ እያየለ መጣ፡፡
በዚህ ወቅት ደግሞ ሊታመን በማይችል ዋጋ፣ የሰፊ መሬት ባለቤት ሊያደርገው የሚችል ዕድል አገኘ፡፡ አንድ ሺህ ሩብል ብቻ የሚከፍልበትን መሬት መርጦ፣ ለክቶና በቃኝ ብሎ የመወሰን መብት ነበረው፡፡ በዚህ መብት ውስጥ የተሰጠው ግዴታ ግን ነበር፡፡ የሚፈልገውን መሬት መርጦ ለመጨረስ፣ ፀሐይ ስትወጣ ጉዞ የጀመረበት መነሻ ላይ ጀምበር ስትጠልቅ መድረስ አለበት፡፡ የሚያየውን ለም መሬት ሁሉ ባለቤት ለመሆን ከመነሻው እየራቀ ስለሄደ፣ በመልስ ጉዞው ለብዙ ድካምና እንግልት ተዳረገ፡፡ ጀምበር ከመጥለቋ በፊት መነሻ ቦታ ላይ ቢደርስም ነፍስና ስጋው በምድር መኖር የሚያስችል አቅም አልነበራቸውም፡፡ አንድ ሜትር ጉድጓድ ተቆፍሮ እዚያው እንዲቀበር ሆነ፡፡
“ቀላዋጩ ሸረሪት” እና “ላንድ ሰው ምን ያህል መሬት ይበቃዋል?” የሚል ርዕስ ያላቸው ታሪኮች መሰረታዊ ጭብጥ አንድ ነው፡፡ ስስታምና አልጠግብ ባይነት በስተመጨረሻ ጉዳት ማስከተላቸው እንደማይቀር ትምህርት ይሰጣሉ፡፡
የሁለቱ ታሪኮች አቀራረብ ግን ተደራሻቸውን ታሳቢ ያደረጉ ናቸው፡፡ የደራሲ ገብረክርስቶስ ኃይለሥላሴ “የሉሲ ክዋክብትና ሌሎችም” መጽሐፍ፤ ለልጆች የሚዘጋጁ መፃሕፍት እንዴት መቅረብ እንዳለባቸው ማሳያ ሆኖ ሊቀርብ ይችላል ያልኩት በዚህ ምክንያት ነው፡፡