Administrator

Administrator

በተለያዩ ከተሞች በራሳቸው፣ በባለቤታቸውና በልጆቻቸው ስም 17 ቦታዎችንና ቤቶችን ይዘዋል ከሚለው ክስ ነፃ ሆነዋል፡፡
ከባለቤታቸው ጋር ምንጩ ያልታወቀ 490ሺ ብር በባንክ አንቀሳቅሰዋል ከሚለው ክስ ነፃ ናቸው ተብሏል

የቀድሞው የቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል ርዕሰ መስተዳድር አቶ ያረጋል አይሸሹም፤ በፀረ ሙስና ኮሚሽን ከቀረቡባቸው አምስት ክሶች መካከል በአንዱ ብቻ “ጥፋተኛ ናቸው” የተባሉ ሲሆን፣ ምንጩ ያልታወቀ ሃብት አካብተዋል በሚል ከቀረበባቸው ክሶች ነፃ ሆኑ፡፡
አቶ ያረጋል አይሸሹም እና የትምህርት ቢሮ ሃላፊ የነበሩት አቶ ሃብታሙ ሂካ፣ ከሁለት የግል ድርጅት ሃላፊዎች ከአቶ ጌዲዮን ደመቀና ከቶ አሰፋ ገበየ ጋር “ጥፋተኛ ናቸው” የሚል ውሳኔ የተላለፈባቸው፤ ለሦስት የትምህርት ተቋማት ግንባታ ከወጣው ጨረታ ጋር በተያያዘ ክስ ነው፡፡ ህገወጥ የጥቅም ግንኙነት በመፍጠር  ለመምህራን ኮሌጅ፣ ለአዳሪ ት/ቤት እና ለቴክኒክና ሙያ ማሰልጠኛ ተቋማት የግንባታ ጨረታ ከመንግስት መመሪያ ውጪ እንዲከናወን አድርገዋል በሚለው ክስ 4ቱ ተከሳሾች ጥፋተኛ ሆነው እንደተገኙ የከፍተኛው ፍ/ቤት ችሎት ሐሙስ እለት ገልጿል፡፡ 

አቶ ያረጋል እና አቶ ብርሃኑ ለተቋማቱ ግንባታ  የተመደበው ገንዘብ ከፍተኛ መሆኑን እያወቁ በግልጽ ተወዳዳሪዎችን ጋብዘው ማጫረት ሲገባቸው፣ የሶስቱንም ፕሮጀክቶች የዲዛይን፣ የቁጥጥር እና የኮንትራት ጨረታ በህገወጥ መንገድ ለጌዲዮን ደመቀ አማካሪ ድርጅት በጥቅሉ በ250ሺህ ብር ሰጥተዋል ይላል ፀረ ሙስና ኮሚሽን ያቀረበው ክስ፡፡ አቶ ያረጋል ስልጣናቸውን ያለ አግባብ በመጠቀም ጨረታዎቹ  አቶ ሃብታሙ በሚመሩት የትምህርት ቢሮ በኩል እንዲከናወኑ አድርገዋል የሚለው የኮሚሽኑ ክስ፣ መመሪያ ከሚፈቅደው ውጪ ስራው  በ “ውስን ጨረታ” እንዲከናወን በደብዳቤ ትዕዛዝ አስተላልፈዋል ብሏል፡፡  ለዚህ ወረታም አቶ ያረጋል ከ3ኛ ተከሳሽ ከአቶ ጌዲዮን ደመቀ፤ 50ሺህ ብር እንዲሁም አቶ ሃብታሙ 75ሺህ ብር እጅ መንሻ መቀበላቸው በክሱ ተገልጿል፡፡
“ጌዲዮን ደመቀ አማካሪ ድርጅት” ፕሮጀክቶቹን የመምራት አቅም እንደሌለው እያወቁ ውል የፈረሙት አቶ ጌዲዮንና ወኪላቸው አቶ አሰፋ ገበየሁ፤ ስራውን ለ5 ዓመታት በማጓተት መንግስትን ለ2.8 ሚ.ብር ተጨማሪ ወጪ ዳርገዋል ብሏል - የፀረ ሙስና ኮሚሽን፡፡

ፍ/ቤቱም በአራቱ ተከሳሾች ላይ የጥፋተኝነት ውሳኔ ሰጥቷል፡፡ ባለስልጣናቱና ፕሮጀክቶቹን እንዲመራ የተደረገው አማካሪ ድርጅት፤ በህገወጥ የጥቅም ትስስር፣ የትምህርት ተቋማቱን ግንባታ ለሦስት ድርጅቶች ሰጥተዋል የሚለው ፀረ ሙስና ኮሚሽን፤ የሚመሩት “ጋድ ኮንስትራክሽን” በ40 ሚ. ብር የአዳሪ ት/ቤትና በ18ሚ ብር የመምህራን ኮሌጅ እንዲገነባ፣ አቶ መክብብ የሚመሩት ንብረት ለሆነው “ኮለን ኮንስትራክሽን” ደግሞ በ17 ሚ. የቴክኒክና ሙያ ተቋም እንዲገነባ በመስጠት ስራው አጓትተዋል ብሏል፡፡
አቶ ያረጋል አይሸሹም ከዚህ ክስ ነፃ መሆናቸውን ፍ/ቤቱ ገልፆ፣ የትምህርት ቢሮ ሃላፊና አራቱ የግል ድርጅት ሃላፊዎች ግን ጥፋተኛ ናቸው በማለት ወስኗል፡፡

ሌላኛው ክስ፣ አቶ ያረጋል፣ እንዲሁም የትምህርት ቢሮ ሃላፊውና ወንድማቸው ምንጩ ያልታወቀ ሃብት አካብተዋል የሚል ነው፡፡
ርዕሠ መስተዳደር በነበሩበት ወቅት ደሞዛቸው 4500 ብር እንደነበረና ከዚያም  የፌደራል የህብረት ስራ ኤጀንሲ ዋና ዳይሬክተር በመሆን ሲሠሩ 5670 ብር ደሞዝ ይከፈላቸው እንደነበረ የሚገልፀው የኮሚሽኑ ክስ፣ ከገቢያቸው ጋር የማይመጣጠን ሃብት አካብተዋል በማለት ከሷቸዋል፡፡

አቶ ያረጋል በራሳቸው ስም በአዲስ አበባ በተለያዩ ከተሞች አራት ቦታዎችንና ቤት ይዘዋል የሚለው የክስ ዝርዝር፣ በባለቤታቸው ስም ደግሞ በ7 ሚሊየን ብር የሚገመት ሆቴልና ድርጅት እንዲሁም ስምንት ቦታ፣ የንግድ ሱቆችና ቤቶችን ቦታዎችን በተለያዩ ከተሞች ይዘዋል ይላል፡፡ በቤንሻንጉል ውስጥም በሁለት ልጆቻቸው ስምም 5 ቦታዎች ይዘዋል፤ በኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ሁለት ቅርንጫፎች በራሣቸው እናበባለቤታቸው ስም ከ490 ሺ ብር በላይ አንቀሳቅሰዋል ብሏል - ፀረ ሙስና ኮሚሽን፡፡

የባለስልጣናት ሃብት ምዝገባ ሲከናወን ሃብታቸውን ሙሉ በሙሉ አላሣወቁም የተባሉት አቶ ያረጋል፤ “ምንጩ ያልታወቀ ሃብት አካብተዋል” የሚለውን ክስ በበቂ ማስረጃ መከላከል በመቻላቸው በነፃ እንዲሰናበቱ ፍ/ቤቱ ወስኗል፡፡

የትምህርት ቢሮ ሃላፊውም እንዲሁ ከወንድማቸው ጋር ከተመሳሳይ ክስ ነፃ ሆነዋል፡፡ ፍ/ቤቱ በሁሉም ክሶች ላይ ውሳኔ ያስተላለፈበትን ባለ 170 ገጽ ትንተና በንባብ ለማሰማት ሁለት ቀን ፈጅቶበታል፡፡
የጥፋተኝነት ውሳኔ በተሰጠባቸው ክሶች ላይ ከከሳሽ እና ከተከሳሽ የቅጣት አስተያየት ለመቀበል ለህዳር 26 ቀን ተቀጥሯል፡፡

በአስረስ አሰፋ ተፅፎ በድንቅስራው ደረጄ እና ያሬድ መንግስቴ የተዘጋጀው “የእኔ እውነት” የተሰኘ ትያትር ከህዳር 14 ጀምሮ በዓለም ሲኒማ ለተመልካች እንደሚቀርብ ተገለፀ፡፡ ትያትሩ ከአንድ አመት በላይ ተደክሞበታል ያሉት አዘጋጆቹ፤ ዘወትር ቅዳሜ ከቀኑ 10 ሰዓት እንደሚታይም አስታውቀዋል፡፡ የትያትሩ ደራሲና ፕሮዱዩሰር አለም ሲኒማን የመረጡትን በመንግስት ትያትር ቤቶች ወረፋው አታካች በመሆኑ ነው ብለዋል፡፡ “ዓለም ሲኒማ ቀና ትብብር አድርገው ወዲያው ነው የፈቀዱልን፤ በቦሌ መንገድ ግንባታ ምክንያት ዘገየ እንጂ አምና ነበር የሚከፈተው” ሲሉም አክለዋል፡፡
በትያትሩ ላይ በ“ሰው ለሰው” የቴሌቪዥን ድራማ የምትሰራውን አርቲስት ምስራቅ ወርቁን ጨምሮ ተዘራ ለማ፣ ዳዊት ፍቅሬ፣ ጥሩዬ ተስፋዬ፣ ቢኒያም ፍቅሩ፣ አስረስ አሰፋ፣ ፍቅሩ ባርኮ እና እምነት ከፈለ ተውነውበታል፡፡

ግማሽ-መንገድ መሄድ ይቅር እንዝለቅ እስከጐሉ ጫፍ
ድጋፍ የለም በግማሽ-አፍ’ ከልባችን እንደግፍ!
የወረት ነው የሚመስል-ካሸናፊ ጋራ እፍ-እፍ
አኪሩ ሲዞር ማቀርቀር-ተሸናፊን ረግጦ ማለፍ!
መቼ በኳስ ብቻ ሆነ - ታይቷል በሌላም ምዕራፍ፡፡
ቋሚ እንሁን እንጽና’እንጂ ከእሳት ወደ በረዶ
መወንጨፍ ከጽንፍ ወደ ጽንፍ
ክñ አመል ነው ዥዋዥዌ-ዛሬ ጓዳ@ነገ ደጃፍ”
ስናገባ ብቻ ዘራፍ!
ስንሸነፍ ጉልበት ማቀፍ!
ሲሞቅ እንደ እንፋሎት መትነን@
ሲበርድ እንደግዑዝ ነገር’ፍፁም ዲዳ በድን መሆን
እሪ ስንል ጐል አግብተን’ያመት-ባል ገበያ መስለን@
በለስ ነስቶን ድል ባይቀናን
ሬሳ የወጣው ቤት መሆን@
ኧረ ጐበዝ! ቋሚ እንሁን !
ገብቶ መፋለም ቢያቅተን
መደገፍ እንዴት ይጥፋብን?!
ከፊልሙ እንዳልተዋደደ
ከግብሩ እንዳልተዋሃደ
ከትወናው ጋራ ሠምሮ’ወጥ ሆኖ አብሮ እንዳልሄደ
ከቦክስ ኋላ እንደሚመጣ’የቀሽም ፊልም አጃቢ ድምጽ
ከድርሰቱ እንደተፋታ’እንዳላማረ ኮሾ አንቀጽ
ሙሉ ጨዋታ መደገፍ’መጮሁ እንዴት ያቅተን?
በቴፕ አፍ የተፈጠረ’የዲጄ ነው እንዴ ድምፃችን?
ባገርም ጉዳይ ይሄው ነው፡-
ቅጥ-አንጣ በድላችን
ሲበልጡን ቆፈን አይያዘን-
መቼም መቼም የትም ቢሆን
ሙሉ ጊዜ ቋሚ እንሁን! እናግዝ ልጆቻችንን!
መቼም ኢትዮጵያዊነትን’የውጪ ባዕድ አልሰጠን
እኛው ውስጥ የበቀለ እንጂ’ “የዲጄ” አይደለም ድምፃችን
ብንሸነፍም እኛው’ብናሸንፍም እኛው ነን!
በወረት አንለዋወጥ’እንደግፍ ከልባችን!
እናግዝ አገራችንን!!
(ለኢትዮ-ናይጄሪያ የኳስ ፍልሚያና ለኢትዮጵያውያን ደጋፊዎች) ኀዳር 2 ቀን 2006 ዓ.ም

Monday, 18 November 2013 11:37

አስማተኞቹ እና ሚስጢራቸው

እኔ የተረዳሁትን ማንም ስላላወቀ እንጂ ሀሳቡ ምንም አዲስ ነገር የለውም፡፡ ንግድ ማለት ቅይይር ማለት ነው፡፡ እንደ ልዋጭ። አንዱን እሴት ትቀበልና በእሱ ፋንታ ሌላውን ትሰጠዋለህ፡፡ ከልውውጡ የምታተርፈውን ነገር (እሴት) መሰብሰብ እና እንደገና በትርፍ ለመለወጥ መሞከር፡፡ ነጋዴ የመሆን ትርጉሙ በአጭሩ ይሄ ነው፡፡
የሚለወጠው ነገር የሚፈለግ መሆን አለበት፡፡ በዚህ በጨፈገገ ትውልድ ላይ እንደ ሳቅ የሚያስፈልግ ነገር የለም፡፡ ሳቅ ውስጡ የሌለው ማንም የለም፡፡ ሳቅን ፍለጋ ግን ገንዘቡን ከፍሎ “ኮሜዲ ሾ” ይገባል። ኮሜዲያን እንደ “አባ ገና” በትልቅ ስልቻ የሳቅ ገፀ በረከት ይዞ የሚዞር ይመስለዋል ታዳሚው፡፡ ግን ትልቅ ስልቻ ይቅርና ኪሱን የሚሞላ ሳቅ እንኳን ይዞ አይመጣም - እንዲያውም በተቃራኒው በኪሱ ያለው ለቅሶ ነው፡፡ እነሱ ታዳሚዎቹ በውስጣቸው ይዘው ያልመጡትን ሳቅ ኮሜዲያኑ ሊሰጣቸው አይችልም።
ኮሜዲያኑ አስማተኛ ነው፡፡ ማስመሰል ነው ስራው፡፡ ከተመልካቹ ሆድ ውስጥ ያወጣውን ሳቅ ከራሱ ሆድ ያፈለቀው አስመስሎ ማቅረብ፡፡ እኔ የገባኝ ሀሳብ ይሄ ነው፡፡ ሀሳቡን ተጠቅሜ የልዋጭ ሰራተኛ ሆንኩ፡፡ ከሰው ውስጥ የተደበቀውን ነገር ግልፅ አድርጌ መልሼ እሸጥለታለሁ፡፡ በሚስጥር፡፡
ሚስጥሩ፡- “If you don’t bring it here, you won’t find it here!” የሚል ቢሆንም፤ ሚስጥሩን ለታዳሚዬ ከገለፅኩለት አስማቴ ይነቃል፡፡ ሲነቃ፤ ጥበብ መሆኑ ይቀራል፡፡ ተራ የወሮበላ ማጭበርበር ይሆናል፡፡ መንገዱን ሳልገልፅ፤ መነሻውን እና መድረሻውን ብቻ ይፋ በማድረግ አስማቴን እሰራለሁ፡፡
መነሻው ይሄ ነው፡፡ መነሻው እንዲህ ነው። ሁሉም ሰው የሚፈልገው ነገር አለ፡፡ አንዳንዱ መሳቅ ነው የሚፈልገው፤ ሌላው ማዘን፣ ሌላው ማፍቀር፣ ሌላው መክበር ወይንም መከበር … ሁሉም የሚፈልገው እና ሊያሟላው ያልቻለ አንድ ፍላጐት አለው፡፡ ያ ነው መነሻዬ፡፡ ከመነሻው እስከ መድረሻው ያለው መንገድ የእኔ ሚስጢር ነው። መድረሻው ሁሉንም እንደየፍላጐታቸው መንካት መቻል ነው። መሳቅ የፈለገው ስቆ፣ ማልቀስ የፈለገው አልቅሶ፣ ማፍቀር የፈለገ ፍቅሩን አግኝቶ … ወደ ቤቱ እንዲሄድ ማድረግ፡፡ መነሻው ላይ ቃል እገባለሁ። ፍላጐቶች ሁሉ ስኬታቸውን እንደሚያገኙ፡፡ መድረሻው ላይ ብር እቀበላለሁ፡፡ ፍላጐታቸውን ከእነሱ ጋር ላገናኘሁበት፡፡
ጥበብ እና አስማተኝነት የደላላነትም ስራ ነው። ፈላጊ እና ፍላጐቱ የሚገናኙበት ምስጢር ግን ከእኔ ጋር ተደብቆ ይቆያል፡፡ የእኔ አስማተኝነት ያለው ሚስጢሩን እስከጠበቅሁ ድረስ ብቻ ነው። ከባድ የሚመስሉ ነገሮች ከብደው የሚቆዩት የክብደታቸው ምክንያት ሳይገለፅ እስከቆየበት ጊዜ ድረስ ነው። ሁሉም ሚስጢር ሲጋለጥ አስቀያሚ እና ተራ ይሆናል፡፡ የኔ ሚስጢር ደግሞ በጣም ቀላሉ ነው። መስታወት ፊት ፈላጊውን ማቆም ነው፡፡ ራሱን በመስታወቱ እየተመለከተ… ግን መመልከቱን እንዳያውቅ በእኔ አማካኝነት የራሱ ምስል ነፀብራቅ እንዲታየው አደርጋለሁ፡፡ መሳቅ የፈለገ ደንበኛዬ ራሱን በእኔ ትርጓሜ ውስጥ ያያል፡፡ ከራሱ የማንነት ምስል በላይ የሚያስቅ ነገር ምን አለ?
ማልቀስ ለፈለገውም ተመሳሳይ ነው፤ ከራስ ምስል በላይ የሚያስለቅስ ነገር ምን ይኖራል? … ግን ያጣውን ነገር ራሱ እንዳያገኝ፣ እኔ በእሱ እና የራሱ ምስል ነፀብራቅ መሀከል ቆሜ አስተረጉምለታለሁ። የራሱ ምስል በእኔ አማካኝነት ሲተረጐም ከማናደድ እስከ ማሳቅ፣ ከማሳቀቅ እስከ ማራቀቅ … ከተስፋ መቁረጥ እስከ ተስፋ ማግኘት ሊለዋወጥ ይችላል። አስማቴም ይኸው ነው፡፡ የጥበብ አስማት ሚስጢር።
ባለ ፍላጐቱ በራሱ አይን ነፀብራቁን ቢመለከት የሚያየው ፍላጐቱን እንጂ መድረሻውን አያይም። ራሱን በራሱ አይን ሲመለከት ጉድለት እንጂ ሙሉነት አይታየውም፡፡ ሁሉም ሰው ለራሱ እይታ ጉድለት ነው፡፡ እንደአጋጣሚ ሙሉ ቢሆን እንኳን ጉድለት ነው ለራሱ አይን የሚታየው፡፡ ስለዚህ አስማተኛ ያስፈልገዋል፡፡ ጉድለቱን ሞልቶ የሚነግረው። ሙሉነቱን ይዤ የምመጣው ከሌላ ቦታ አይደለም፡፡ ከራሱ ኪስ አውጥቼ ነው ወደ ፍላጐቱ የሚያደርሰውን ክፍያ የምሰጠው፡፡ ግን አስማት እንደመሆኑ፣ የሞላሁለትን ፍላጐቱን ይዞ ከትያትር ቤቱ ወጥቶ የወል ቤቱ ሲደርስ፣ ከአስማቱ በፊት ወደነበረው ማንነቱ ይመለስና ጐዶሎ ይሆናል፡፡
ሳንድሬላ በአስማተኛዋ አያቷ (አክስቷ) አማካኝነት ከአመዳም ገረድነት ወደ እፁብ ድንቅ ልዕልትነት ተቀየረች፡፡ አያቷ (አክስቷ) የከወነችው አስማት እኔ ያወራሁላችሁን ነው፡፡ ሳንድሬላን የቀየረቻት… ስለ ራሷ ያላትን አመለካከት በመቀየር ነው፡፡ ገረዲቱ በራሷ ፊት ስትቆም ይታያት የነበረውን ምስል ወደ ልዕልት ምስል ቀየረችው፡፡ ሳንድሬላ ውስጥ ቀድሞውኑ ልዕልት የመሆን ፍላጐት ወይንም ምኞት ባይኖር ኖሮ፣ በአስማተኛዋ አያቷ ሀይል ሆነ በጠንቋይ ድግምት ልትፈጠር፣ ልትለወጥ አትችልም ነበር፡፡ ፍላጐቷን እና መፍትሄዋን ከእራሷ ውስጥ አውጥታ አለበሰቻት፡፡ ከተቀዳደደ ልብሷ ውስጥ በእንቁ የተንቆጠቆጠ ቀሚስ በአስማት አማካኝነት አለበሰቻት፡፡ ከራስ ምስሏ ጋር የተቆራኙትን አይጦች፣ በነጫጭ ፈረሶች ተካችላት፡፡ ዱባውን ደግሞ ወደ ሰረገላ፡፡
በአስማተኛ አያቷ የተለወጡ ማንነቷን ይዛ ልዑላኖቹ ጋር ተቀላቀለች፡፡ ህልሟን በጥበብ አስማት እውን አድርጋ ልዑል አፈቀረች፡፡ ስድስት ሰአት ከሌሊቱ ሲሆን … አስማቱ ወደ ቀድሞው ተፈጥሮው ተቀየረ፡፡ አይጥም አይጥ፣ ዱባውም ዱባ … ሳንድሬላም ተመልሶ ተራ አመዳም ገረድ ሆነች፡፡ አስማት እና ተአምር የሚለያዩት አንዱ ወደነበረበት ይመለሳል፡፡ ሌላኛው አስማት ሆኖ ይቀራል፡፡
ጥበብ የራስን ምስል ከጉድለት ወደ ሙሉነት የምትቀይር መስታወት ናት፡፡ በመስታወቷ የሚታየውን ምስል ወደ ታዳሚው ፍላጐት የሚቀይረው ሰው ጥበበኛ ይባላል፡፡ ራስን በራስ የሚቀይር ልዋጭ እንደማለት ነው፡፡ ራስን በራስ አማካኝነት የሚቀይረው ባለሞያ ጥበበኛ ተብሎ ሲጠራ መስማት የተለመደ ቢሆንም፣ ዋናው ስሙ ግን አስማተኛ ነው፡፡
የጥበብ ታዳሚው ራሱን ይዞ ወደ ትርዒቱ ስፍራ ይመጣል፡፡ በፍላጐት ተሞልቶ፡፡ የትርዒቱ ስፍራ የስዕል ሸራ፣ የመጽሐፍ ገፆች ወይንም የትያትር መድረክ ሊሆን ይችላል፡፡ ከራሱ ውስጥ ስሜቶቹን እንደ ክራር እየቃኘ … ፍላጐቱን፣ ምኞቱን ከጉድለት አውጥቶ ሙሉ ያደርገዋል - ባለ ሞያው ከተራ ቃላቶች ውስጥ ለእያንዳንዱ ታዳሚው የሚሆን መፍትሄ ያገኛል፡፡
ማልቀስ ለሚፈልገው ለቅሶ … መሳቅ ለሚፈልገው ሳቅ፡፡ የሚስቅ እና የሚያለቅሰው ታዳሚው ራሱ ቢሆንም …ሳቁና ለቅሶው ግን በራሱ ላይ ነው፡፡ በራሱ አማካኝነት ነው፡፡ በትክክል የሚገጣጥመው ጥበበኛ ካገኘ… ማንኛውም ሰው በውስጡ ሙሉነት አለ፡፡ ልዕልቷ ሳንድሬላን ትሆናለች፤ በአስማተኛው አማካኝነት፡፡ ሳንድሬላም ልዕልቷን፡፡
ግን አሁን አሁን፤ አስማተኛ የመሆን ሳይሆን አስማተኛን የማጋለጥ ፍላጐት እያደረብኝ ነው፡፡ የቆዩ የአስማት ሚስጢሮች ካልተጋለጡ አዳዲሶቹ አይፈጠሩም፡፡ ጠንከር ያሉ ወይንም ፍቻቸው ቶሎ የማይደረስበት መንገዶችን ለመፍጠር ቀላሎቹ የአስማት ሚስጢሮች “tricks” መጋለጥ አለባቸው። እውነተኛ አስማተኛ የሚለየው … ከፍላጐት ወደ ግኝቱ በሰው ስሜት መሰላል አማካኝነት ሲወጣጣ … የተወጣጣበትን መሰላል በመደበቁ አይደለም። መንገዱን እየገለፀም… ማንም መንገዱን ተከትሎ እሱ የከወነውን አስማት መስራት ሲያቅተው ነው፡፡ ሚስጢርን መጠበቅ ብቻ ሳይሆን መግለፅም አዳዲስ አስማቶች እንዲፈጠሩ በይበልጥ ያግዛል፡፡
ሚስጢሩ ቢገለፅ እንኳን ማንም ማከናወን የሚችለውን አስማት እየሰሩ እውነተኛ ጥበበኛ መሆን አይቻልም፡፡ የወል የአስማት ትርዒት፣ ይትባህል እንጂ ጥበብ አይሆንም፡፡ ሚስጢሩ ቢገለጥም ማከናወን ከባድ የሆነ አስማት ሳንድሬላን አንዴ ልዕልት ካደረጋት በኋላ፣ ከሌሊቱ ስድስት ሰአት ላይ ወደ አመዳም ገረድነት (ብቃት ባለው አስማተኛ በተሰራ ጥበብ ላይ) አትለወጥም፡፡ ልዕልት እንደሆነች ትቀራለች፡፡
መለወጧ ባይቀር እንኳን፤ በሰአታት ውስጥ ሳይሆን ብዙ ዘመናት ይፈጅባታል፡፡ ለምሳሌ ዶስትዮቪስኪ እንደዛ አይነት አስማተኛ ነው የሚሉ አሉ፡፡ እኔ ደግሞ ኧ. ሄሚንግዌይ አስማቱን የሚሰራበት ሚስጢር ቢገለፅ እንኳን ማንም ሊያከናውነው የማይችል የአስማት አይነት ነው የሚሰራው ባይ ነኝ፡፡
የአስማታቸው ሚስጢር ሲጋለጥ፤ ሁሉም በየቤቱ ደብዳቤ ለመፃፍ የሚጫጭረውን ያህል ጥበብ ፈጥረው የተገኙም አሉ፡፡ ቀላሉን የአስማት ሚስጢር በማጋለጥ… ከባባዶቹ እንዲፈጠሩ መንገድ ማመቻቸት ነው… ከቅርብ ጊዜ ወዲህ የጀመርኩት ስራ፡፡ እናም እላለሁ፤ አስማተኛ አስማቱን በከረጢት ይዞ አይዞርም፡፡ አስማቱን የሚፈጥረው ከታዳሚዎቹ ፍላጐት እና ነፀብራቅ በመነሳት ነው፡፡ ታዳሚዎቹ ሀዘን፣ ደስታ፣ ተስፋ እና አንዳች ፍላጐት በውስጣቸው ቀብረው ወደ አስማተኛው ባይመጡ አስማተኛው ብቻውን የሚከውነው አንዳች ነገር ባልኖረው ነበር፡፡ If you don’t bring it here you won’t find it here! ይላችኋል፤ ጥበበኛው ባዶ ከረጢቱን እያሳየ፡፡
የአስማተኛው ጥሬ እቃዎች እናንተ ናችሁ፡፡ ጥሬ እቃዎቹን ከተራ ወደ እፁብ ድንቅነት የሚቀይርበት መንገድ ነው ሚስጥሩ፡፡ ጥበበኛ ሚስጢረኛ ነው። ምርጥ ሚስጢረኛ ግን ሚስጢሩን የሚደብቅ ሳይሆን ለመግለፅ የሚሞክር ነው፡፡ ሚስጢረኛ የሆነበትን ሚስጢር ለመፍታት በሚያደርገው ሙከራ እና ሂደት …እናንተን ከፍላጐታችሁ ወደ ግባችሁ ያደርሳችኋል፡፡ ሚስጢሩን ለመፍታት በሚሞክርበት ጊዜ ነው አስማቱ የሚፈጠረው፡፡ ከከባድ ሚስጥሮች ፍቺ የሚገኝ አስማት ነው ልዕለ - ጥበብ፡፡ የልዕለ ጠቢብም አሻራ:- ሚስጥርን መግለፅ እንጂ መደበቅ አይደለም፡፡ በተገለፀ ቁጥር የሚደበቅ ሚስጥርን ለመፍታት ጠንካራ አስማተኞች ያስፈልጉናል፡፡ እውነተኛ አስማተኞች፡፡ ካርታን ደርድሮ “ቀዩዋን ያየ” እያሉ የሚያጭበረብሩት…እውነተኛም፣ ሚስጥረኛም አስተማኛም አይደሉም። ምናልባት “ወሮበላ” ሊሆኑ ይችላሉ፡፡ ግልፁን ሚስጢር የሚያደርግ እና ሚስጢሩን ለመግለፅ በሚሞክር መሀል የሰማይ እና የምድር ያህል ርቀት አለ፡፡ አንደኛው ወሮ በላ ይባላል፡፡ ሌላኛው አስማተኛ ነው፡፡ አስማተኝነትን ከሌላ አስማተኛ በመማር ሚስጢሮችን እና አፈታታቸውን አጥንቶ፣ “የጥበቡ ጥሪ አለኝ” የሚል ሊጀምር ይችላል፡፡
አዲስ አስማት መፍጠር ካልቻለ … ወይንም ካልሞከረ ግን በስተመጨረሻ የሚገባው ወደ ማጭበርበሩ ነው፡፡ ቀላልን ሚስጢር ከባድ አስመስሎ ወደመደበቁ፡፡


22ሚ. ብር የሚፈጅ “የብዕር አምባ” ግንባታ ይጀመራል
አዲሱ የኢትዮጵያ ደራሲያን ማህበር የስራ አስፈፃሚ ኮሚቴ፤ መላው የአገሪቱ ደራሲያንና የድርሰት ወዳጆች ከስነ ጽሑፍ እድገት ጐን እንዲቆሙ ጠየቀ፡፡
በቅርቡ የተመረጠው የደራስያን ማህበር አመራር፤ ትላንት በፅ/ቤቱ በሰጠው መግለጫ፤ ማህበሩ ለግማሽ ክፍለ ዘመን ያካበተውን ልምድና ያከናወናቸውን ተግባራት መሠረት በማድረግ፣ ከዘመን ዘመን ማህበሩን ሲፈታተኑ የቆዩ ማነቆዎችንና ተግዳሮቶችን በማስወገድ በቁርጠኝነት እንደሚሠራ አስታውቋል፡፡ አዳዲስ የአስተሳሰብና የአሠራር አቅጣጫዎችን ቀይሶ፣ አባላቱን ከዳር እስከዳር በማንቀሳቀስ ማህበሩን ወደ ላቀ የእድገት ደረጃ ለማድረስ ቆርጦ መነሣቱንም ገልጿል፡፡
የማህበሩ ስራ አስፈፃሚ ቀዳሚ የትኩረት እንቅስቃሴ አቅጣጫዎቼ ናቸው በማለት ከዘረዘራቸው መካከል፤ ከ22 ሚ. ብር በላይ ወጪ ይጠይቃል የተባለው “የብዕር አምባ” ግንባታ እንዲጀመር ማድረግ፣ የማህበሩን ገቢ በተለያዩ እንቅስቃሴዎች ማስፋትና የማህበሩን የህትመት ውጤቶች በብዛትም በጥራትም መጨመር የሚሉት ይገኙበታል፡፡ በየክልሎቹ ያሉትን ቅርንጫፍ ጽ/ቤቶች ቁጥር ለማሳደግ እንደሚሠራና ብዕርተኞች የሚዘከሩባቸውን የተለያዩ ዝግጅቶች እንደሚያካሂድ የገለፀው ማህበሩ፤ የመጽሐፍት ማከፋፈያና መሸጫ መደብሮች፣ በአዲስ አበባ ማዕከላዊ ቦታዎች ላይ ለመክፈት እጥራለሁ ብሏል፡፡ የማህበሩን ጥረት ለማገዝም የድርሰት ወዳጆች ከጐኑ እንዲቆሙ ጥሪ አቅርቧል፡፡

              “እንደገና ፊደል እንደገና” የሚያሰኘን እያረፈ የሚነሳው የፊደል ማሻሻል ጥያቄ ጉዳይ ነው። ጥያቄውን የሚያነሱት ምሑራን ምክንያታቸው ምንድነው? በተለይ ጐልቶ የሚነሳው የሞክሼ ፊደላት ጉዳይ ነው፤ እነዚህንስ መነካካቱ ያስፈለጋቸው ለምንድነው የሚለውን በቅድሚያ መመልከቱ ተገቢ ይመስላል፡፡ ከሞክሼዎቹ የተወሰኑትን የማስወገዱ እርምጃ የሚያስከትለውን ጉዳት/ጉድለት ደግሞ ከዚያ በኋላ እንመለከተዋለን፡፡ 
አሁን እስኪ ሞክሼ ፊደላቱን ለማጉደል ምን ምን ዓይነት ምክንያቶች እንደሚሰሙ እያነሳን እንመልከት-
አንድ ድምጽ፣ አንድ ምልክት
ትክክል፡፡ አንድ ምልክት አንድን ድምጽ ወይም ክፍለ ቃል፣ አንድ ክፍለ ቃልም በአንድ ምልክት መወከል አለበት፡፡ ማንም ሊገምት እንደሚችለው፣ እነዚህ ምልክቶችም እያንዳንዳቸው አንድን ድምጽ ለመወከል የተሠሩ ናቸው፡፡ ብዙዎች አንዱን ድምጽ ሊወክሉ አልተሠሩም፡፡ በእርግጥም አልነበሩም፡፡
እንዲህ የሆነው ከጊዜ በኋላ ነው፡፡ ኪዳነ ወልድ ክፍሌ ከአባ ሰላማ ወዲህ ነው ይላሉ፡፡ ግን አይደለም፡፡ ከዚያ ወዲህ፡፡ ቢያንስ በጽሕፈት ላይ ሲቀያየሩ አይታዩም፡፡ ድምፃቸው አንድ ኾነ ተብሎ በጽሕፈትም የአንዱን ለአንዱ ማድረግ ይታይ ነበረ፡፡ ከዚህም ሌላ በአባ ሰላማ ጊዜ ኅርሙኅ ተጨምሯል። እነዚያ አንድ እየኾኑ ይሕን ይጨምራሉ አይባልም። ደሞም የዚህኛውም ድምጽ አንድ ሆኖ ተገኝቷልና በአባ ሰላማ ጊዜ ሲጨመርም አንድ ድምጽ ይዞ ተጨመረ ማለትን ይመስላል፡፡
በሚገባ የታወቀው ይህ የድምጽ አንድነት የታየው፣ በመጽሐፈ ጥበብ እንደተገለፀው፣ ከልብነ ድንግል ዘመን ወዲህ ነው፡፡ የአምስት መቶ ዘመን ዕድሜ አለው ማለት ነው፡፡ በዚሁ መጽሐፍ የየራሳቸው ድምጽም ተመዝግቧል፡፡ ፍሬ ነገሩ ግን ድምፃቸው በግዴለሽነት ተመሳሰለ ብሎ እንዲወገዱ መጠየቅ አለበት ወይ? የሚለው ይሆናል፡፡ ይህ ምልክቶቹን ድምጽን ለመወከል የተሠሩ በማድረግ፣ ሥነ ልሣናዊ ዕቃዎች ብቻ በማድረግ፣ ስንፍናን እና ጉድለትን በጉድለት መተካትና ማረም፤ ከሁሉም በላይ ደግሞ ምልክቶቹ ያላቸውን ሌሎች አገልግሎቶችና ውክልናዎች እንዳሉ መጣል መሆኑን ካለማየት የሚመጣ ጥያቄ ነው፡፡ በአጭሩ፣ የሰነፍ፣ የደካማና የታካች አቋራጭ መንገድ ነው፡፡
የፊደላት ብዛት
የፊደላት ብዛት ጥያቄ የሚነሣው ይበልጡን በአጠቃላይ ፊደሉን ከመነካካት ጥያቄ ጋር ነው። ከሞክሼ ፊደላት አንጻር አይደለም፡፡ ምናልባት “ፊደሉም ብዙ ምልክቶች ያሉት ነውና ሞክሼዎቹ ሲቀነሱ ያነንም ጥያቄ ይመልስልናል” በሚል ግንዛቤ እንደ አንድ ነጥብ ይነሳ ይሆናል፡፡ ከዚህ ውጭ ፊደሎቹ የበዙት አንዱን ድምጽ የሚወክሉ ከአንድ በላይ የሆኑ ፊደላት ስላሉ ነው የሚል የለም፡፡
እዚህ ላይ ግን ጠቅላላ በፊደል ላይ የሚነሱ ጥያቄዎችንም ለመመልከት ያህል አንስተነዋል፡፡
የፊደል ብዛት ጥያቄ በአማርኛም ሆነ በግዕዝ የሚጠየቀው ፊደላቱን ካለመለየት የተነሣ ነው። ፊደላት የገበታ እና የርባታ ተብለው ይለያሉ። የየትኛውም ቋንቋ ፊደል ምን ያህል እንደሆነ ሲጠየቅ የሚነገረውም የገበታው ፊደል ብዛት ነው። የኢትዮጵያው ፊደል በዝቷል ሲባል ግን በቁጥር የሚነገረው የገበታው ከርባታው ሳይለይ ነው፡፡ ለምሣሌ፣ የአማርኛውን ብንወስድ ጠቅላላ ብዛቱ ወደ ሦስት መቶ የሚጠጋ ተደርጐ ይነገራል፡፡ ይህም:-
እያንዳንዱ የገበታ ፊደል በ7 ተባዝቶ - 238
ዲቃሎቹ (4x5) = = 20
ፍንጽቆቹ = 21
ጠቅላላ 279 ይሆናሉ፡፡
እንዲህ በመሆኑ በዝቷል ነው የሚሉት። በዝተዋል ተብለው መቆጠር የነበረባቸው ግን እንዲህ አልነበረም፡፡ ለየትኛውም ባለ ጽሕፈት ቋንቋ የፊደላት ብዛት ሲጠየቅ ይህን ያህል ነው የሚባለው የገበታው ፊደል ብቻ ነው፡፡ እንግሊዝኛ 26 ፊደል አለው፤ ግሪክ 28 አለው፡፡
ዓረብ 29 አለው፤ የሩስያ 33 ፊደል የሚባለው የገበታ ፊደሉ ብቻ ተቆጥሮ ነው፡፡ የርባታ ፊደሎቻቸውን/ምልክቶቻቸውን/ እንደ አንድ እየቆጠርን እንጠቁም ቢባል፣ እንደ እንግሊዝኛ ያለው ለአማርኛ ከተቆጠረውም በእጥፍና ከዚያ በላይ የሆነ ብዛት ይኖረዋል፡፡
በኢትዮጵያ ያለው የርባታ ሥርዓት በነ ዳንኤልስ “አቡጊዳ” የተባለው ዓይነት ሆኖ፣ በመሠረታዊው ፊደል ላይ የተለያዩ ጭማሪዎች በማድረግ አንድ ምልክት እየተደረገ የሚሠራ በመኾኑ እነዚያንም ደርቦ በመቁጠር ቁጥሩን ማብዛቱ ተገቢ አይደለም። መሠረታዊዎቹ ስንት ናቸው ብሎ ነው መቁጠር፡፡ በዚህ መሠረት ለግዕዝ 26 ፊደላት፣ ለአማርኛ ደግሞ 34 ፊደላት ብቻ ይኖሯቸዋል፡፡
እንደዚያም ቢኾን የሞክሼ ፊደላቱ ቢቀነሱ ያን ያህል ወደ 300 የተጠጉ ናቸው ካሏቸው ውስጥ ምን ያህሉን ነው የሚቀንሱላቸው?... በአጠቃላይ፣ ከሞክሼ ፊደላቱም አኳያም ሆነ ከሌላ፣ የፊደል ብዛት ጥያቄው ተገቢ ጥያቄ አይኾንም፡፡ ፊደላቱም ብዙ አይደሉም፡፡
የቴክኖሎጂ ውጤት ለኾኑ መጻፊያዎች ቸገረ፡-
ይህ ጥያቄ አስቀድሞ “ታይፕ ራይተር” በነበረበት ወቅት፣ በተለይ መጀመሪያ ላይ እንደ አንድ ችግር ተነስቶ ነበር፡፡ በዚህ ፊደሉን የመነካካት፣ እንዲያውም የመለወጥ ጥያቄ እስከ ማንሳት ድረስ ያሳሰቡት፣ በአስፋው ዳምጤ “ጐምቱ አብዮተኞች” ተብለው የተጠሩ እነ መርስዔ ኀዘን ወልደ ቂርቆስ አንስተውት ነበር፡፡ ይህንን መነሻ አድርጐ የፊደል ነካኪዎችን ታሪክ የጠቃቀሰ የዶ/ር መርሻ አለኸኝ ጥናታዊ ወረቀት፣ ታይፕ ራይተሩ ራሱ ለፊደል እንዲመች ኾነና ፊደሉ ከመቀየር እንደተረፈ ጠቁሟል፡፡ አሁን ደግሞ እንደ አዲስ ለኮምፒውተሩ እንዲመች የሚል ሐሳብ ነው የሚነሳው፡፡ ለኮምፒውተሩ ያልተመቹ ፊደላት ሳይኖሩ ይህን ጥያቄ ለምን እንደሚያነሱት ለማንም አይገባም፡፡ ደግሞም የፊደላቱ ድምፅ አንድ መኾን በቴክኖሎጂው ላይ የሚያመጣው የተለየ ችግር ምን ሊኾን እንደሚችልም አይገባንም። በማንኛውም ቢኾን ስለቴክኖሎጂ ተብሎ ያለው ነገር ይቀነስ ማለት ደግሞ በጭራሽ ተገቢነት አይኖረውም፡፡ ቴክኖሎጂው ለእነዚያ ተብሎ ይሠራል እንጂ፣ እነዚያ ለቴክኖሎጂው አይሠሩም። ለእንግሊዝኛው ወይም ለላቴኑ ፊደላት እንዲኾኑ ተበጁ እንጂ ለቴክኖሎጂው ሲባል እንግሊዝኛው፣ ላቲኑ - ሌላውም በጭራሽ አልተነካም፡፡ ቴክኖሎጂ ያለውን በሚመጥንና በሚያካትት መጠን ይሠራል እንጂ ያለው ነገር ለቴክኖሎጂው ሲባል መሠረቱን እንዲለቅ አይደረግም፡፡ ስለዚህ ጥያቄውን የማይረባና ተገቢ ያልኾነ አድርገን እንጥለዋለን፡፡
የሥነ ጽሑፍ ዕድገት ጥያቄ፡-
“የእናቴ መቀነት አደናቀፈኝ” የማለትም ያህል ይሆናል፡፡ ከፊደላቱ የተወሰኑትን አጉድሎ የየትኛውም ቋንቋ ሥነ ጽሑፍ አልተመነደገም። በሞክሼ ፊደላት ሰበብ ይህ የስነ ጽሑፍ ዕድገት ይጠቀስ እንደኾነ አፍን ሞልቶ መናገር ባይቻልም፣ ከ2005 ዓ.ም ጀምሮ፣ ዘንድሮም የነዚህን የሞክሼ ፊደላትን ነገር የሚያነሳሱት ዶክተር በድሉ ዋቅጅራ፣ በአንድ የመጽሔት ጽሑፋቸው ላይ ፊደላቱ ከገበታው መገኘታቸውን በማማረር፣ “የድሮን ነገር ለመጠበቅ ወግ ሲባል የዛሬው ዘመኑ እንዲጋረድብን /እንዲጨልምብን” መደረግ እንደሌለበት በሚከብድ ኃይለ ቃል የጻፉትን በማሰብ፣ የእነዚህ ፊደላት መኖር እንዲያ ያለ ጽልመት ውስጥ እንደሚጨምረን የታሰበው ምናልባት ከዚህ የሥነ ጽሑፍ ዕድገት ጋር ታስቦ ይኾን እላለሁ፡፡
ይህ የስነ ጽሑፍ ዕድገት ጥያቄ በኢትዮጵያ ቋንቋዎች ጥናት ተቋም አስቀድሞ እንደ አንድ ነጥብ ሲጠቀስ እናስታውሳለን፡፡ ለሞክሼዎቹ ብቻ ሳይሆን በአጠቃላይ በፊደላቱ ላይ ለሚወሰድ እርምጃ የተጠቀሰ ነበር፡፡
የስነ ጽሑፍ ዕድገት ጥያቄ ፊደልን በማጉደልና በመለወጥ ረገድ ከሚነሣ ይልቅ እንዳሉ ቢቀመጡ ከሚናገረው ወገን ቢጠቀስ የበለጠ በተመቸ ነበር። ፊደልን በመነካካት (በመቀየር፣ በማጉደል …) ስነ ጽሑፍ እንዴትም ኾኖ እንደማይበለጽግ ሲታሰብ፣ ጥያቄው ጩኸትን የመቀማት ያህል ኾኖ ይታሰባል። ይልቅስ ዛሬ ድምፃቸው አንድ ኾነ ተብሎ እንዳሻ በመጻፍ የሚታየውን ጉድለት ለማስቀረት፣ የነዚያን አገባብ ለይቶ ዐውቆ፣ ማሳወቅና መጠቀም እንጂ፣ የነዚህ መኖርስ ስነ ጽሑፍን ሊበድለው አይችልም።
ለማጠቃለል፣ በሞክሼ ፊደላቱ ላይ የሚነሳው ጥያቄ ያሉት ሰበቦች እነዚህን የመሰሉ ሲኾኑ፣ አንዳቸውም ግን ሚዛንን ሊያነሱ ቀርቶ እንደ ምክንያት እንኳ ሊቆጠሩ አቅም ያላቸው አይደሉም። ይልቅስ በተቃራኒው፣ “ማሻሻል” በምትል መልካም ቃል የሚታሰበው የመቀየር፣ የማጉደልና ሌላም እርምጃ ቢፈጸም የሚደርሰው ጥፋትና ጉድለት ብሶ እንደሚገኝ ማስተዋል ይገባል፡፡

በዱሮ ጊዜ በአንድ መንደር አራት ክፉ ክፉ አለቆች ይኖሩ ነበር ይባላል፡፡ እነዚህም፤ አቶ ዓለም፣ አቶ ደመና፣ አቶ ሰማይ ነህ እና አቶ በላይ ይባላሉ፡፡
አቶ ዓለም ለምጣም ሲሆን ሰውን ከሥራ ማባረር የሚወድ ቂመኛና ክፉ ሰው ነው፡፡ በማርፈድ ከሥራ ያስወጣል፡፡ ቆማችሁ ስታወሩ አገኘኋችሁ ብሎ ከሥራ ያስወጣል፡፡ ስጠራችሁ ቶሎ አልመጣችሁም ብሎ ከሥራ ያባርራል፡፡
አቶ ዓለም ደግሞ ከባላገር መጥቶ የሠለጠነ፣ ከሁሉ የምበልጥ ነኝ ባይ፣ ትኩስ ዘናጭ ነው፡፡ ሆኖም ሌላው የለበሰው ማናቸውም ልብስ ያስቀናዋል። በዚህ ምክንያት ደህና የለበሰ ሰው ላይ መጮህ ነው፡፡ ሰበብ እየፈለገ መደንፋት ነው!
አቶ ሰማይ ነህ ደግሞ የሁሉ አለቃ ነኝ ባይ ነው፡፡ ዋና ሥራው መጠራጠር ነው፡፡ ምንም ነገር ይስማ “ይቺማ ነገር አላት” ይላል፡፡ አንድ ሰው ለጨዋታ ብሎ ቀና ነገር ሲነግረውም፤ “ከጀርባው ምን አለው? ምን ቢያስብ ነው?” ይላል፡፡
የመጨረሻው አቶ በላይ ነው፡፡ በላይ እንደስሙ የበላይ ነው፡፡ የመሥሪያ ቤቱ የመጨረሻ ጣሪያ እሱ ነው፡፡ ግን መሀይም ነው! የተማረ ሲያይ ደሙ ይፈላል፡፡ “ወረቀት አደለም! ወረቀት አደለም! ዋናው ሥራ ነው! እዚህ ወረቀት እያንጋጋችሁ አትጐለቱ!” ይላል፤ ጠዋት ገና ሥራ ሲገባ!
እነዚህን ሰዎች በቅጡ የሚያውቅ ባለቅኔ እንዲህ ሲል ገጠመ ይባላል
“ዓለም ቡራቡሬ፣ ሁሉን ሰው አታላይ
ደመናውን አልፎ፣ አለ ጥቁር ሰማይ
የተማረው ከሥር፣ ያልተማረው በላይ”
                                                              * * *
የሀገራችን ቢሮክራሲ በመልካም ሰዎች ሳይሞላ መልካም አስተዳደር ማምጣት አዳጋች ነው፡፡ ከመግዛት ባህሪያችን፤ ከአለቅነት ባህሪያችን በፊት ሰው የሚያደርግ ልዩና መልካም ባህሪ ሊኖረን ይገባል፡፡ ለዚህ ደግሞ ከቤተሰብ ጀምሮ ከተኮተኮትንበት ግብረገብነት እስከ ትምህርት ወግ -ማዕረግ ድረስ የሠለጠነ አዕምሮና የበሰለ የህይወት ልምድ ውስጣችን መገንባት ይኖርበታል። ከዚያ፤ በሥራ ዓለም የምናገኘው የዕለት ተዕለት ልምድ፣ ከየሰዉ ጋር ያለንን መስተጋብር (Interaction)፣ ትዕግሥትና ሆደ - ሰፊነት፣ ትህትናና ክህሎት፤ ብሎም የአመራር ብቃት እየሠረፀብን ይመጣል፡፡
በዚህ ላይ ነው እንግዲህ ቅጥ ያለው የፖለቲካ አመለካከት ሲጨመርበት፣ በግድ እኔ ያመንኩትን እመን፣ ያን ካላረክ ጠላቴ ነህ፤ የሚል ሰው አንሆንም፤ የምንለው፡፡ ያመንከውን አምነህ፣ ተቻችለን አንድ መሥሪያ ቤት መኖር አያቅተንም ብለን ማሰብ፤ ጤናማና ዲሞክራሲያዊ አስተሳሰብ ነው። ከማቃቃር ይልቅ ያቀራርበናል፡፡ ከማራራቅ ይልቅ ያስተቃቅፈናል፡፡ ከመጠፋፋት ይልቅ ያስተራርመናል፡፡
በእስተዛሬው የፖለቲካና የማህበራዊ ጉዞአችን ወይ “ብቆጣም እመታሻለሁ፣ ብትቆጪም እመታሻለሁ” ማለት፤ አለበለዚያ ደግሞ “አሸናፊ ነኝ ያለኔ አታውራ”፤ “ተሸናፊ ነህ ስላንተ እንዳይወራ!” እንዳንል ያደርገናል፡፡
መልካም የስፖርት ድጋፍ ባህል መዳበር አለበት፡፡ በስንት ዘመን ዛሬ ያጋጠመንን ዕድል ተመስገን እንበል፡፡ ተጨዋቾቻችን በምንም መመዘኛ ዛሬ የደረሱበት ደረጃ የሚመሰገን ነው፡፡ አንድ ከተመልካቾቻችን የሚጠበቅ ባህል አለ ዘላቂነት የሙሉ ጊዜ ድጋፍ የመስጠት ልምድ! ይሄ በአንድ ቀን ሊሆን የሚችል ባህሪ እንዳልሆነ ግልጽ ነው፡፡ ሆኖም በልቦናችን ይደር ብናሸንፍ ወይም ብንመራ ቴሌቪዢናችንን የበለጠ እንደማንከፍተው ሁሉ፤ ብንሸነፍ ቴሌቪዥናችንን አንዘጋውም፡፡
ከአንድ የጭብጨባና የጩኸት ድጋፍ ድምጽ በአንድ ጊዜ ወደሚደብት የድብርት ድባብ አንግባ፡፡ በየትኛውም ማህበራዊ መስክ፣ ፖለቲካችንን ጨምሮ፤ የሞቅ ሞቅና የለብለብ አካሄድ ደግ አደለም፡፡ ዘላቂ እንሁን በአቋማችን እንግፋ፡፡
አለበለዚየ “ያደሩበት ጭቃ፣ ከጭድ ይሞቃል” ዓይነት ይሆንብናልና በአዎንታዊ ጉዟችን እንግፋ ማናቸውም ውጤት የነገ መንገዳችን መትጊየ ነው፡፡ ፈረንጆች፤ “all that had gone before was a preparation to this; And this is a preparation to this” ይላሉ፡፡ “እስካሁን ያለፍንበት ሁሉ እዚህ ለመድረስ ነበር፡፡ ይሄ ደሞ ለነገ መዘጋጃችን ነው” እንደማለት ነው፡፡
ድል ለዋሊያዎቻችን!

ጋዜጠኛ ነኝ በማለት አጭበርብሯል የተባለው ቻይናዊ የዜድቲኢ ሰራተኛ ነው ተብሏል። ZTE፣ ለስራ ወደ ጅማ የሄደ ሰራተኛ የለንም፤ የተፈላጊውን ማንነት አጣራለሁ ብሏል። በጅማ ከተማ ጋዜጠኛ ነኝ በማለት አጭበርብሯል የተባለው ቻይናዊ ኢንጂነር ዋንግ ዮንግ ለምርመራ እየተፈለገ ሲሆን፣ የጅማ ፖሊስ ተጠርጣሪውን ከአዲስ አበባ ይዞ ለመውሰድ እያፈላለገ ነው።

ዋንግ ዮንግን በሚመለከት የዜድቲኢ የህዝብ ግንኙነት ተወካይ ተጠይቀው በሰጡት ምላሽ፣ ዜድቲኢ ለስራ ወደ ጅማ የላከው ሰራተኛ፤ የለም፤ የተፈላጊውን ማንነት እናጣራለን ብለዋል። ከጅማ ፖሊስ ለቀረበ ጥያቄ የሰራተኛና ማህበራዊ ጉዳይ ሚኒስቴር በሰጠው ምላሽ፣ ዋንግ ዮንግ የቴሌኮም ኢንጂነርና የዜድቲኢ ሰራተኛ መሆኑን ገልጿል። የጅማ ፖሊስ ከአዲስ አበባ ፖሊስ ጋር በመተባበር ተፈላጊውን ተጠርጣሪ ለመያዝ ሲያፈላልግ እንደቆየና ትናንት የዜድቲኢ ተወካዮችን እንዳነጋገረ ታውቋል።

ፖሊስ ዋንግ ዮንግን ለምርመራ ማፈላለግ የጀመረው፣ ጥቅምት አጋማሽ ላይ ጅማ ውስጥ “ጋዜጠኛ ነኝ በማለት አጭበርብሯል” የሚል ጥቆማ ከአካባቢው ነዋሪ ከወ/ሮ ታደለች ተመስገን ከደረሰው በኋላ ነው። ጉዳዩም ከካሳ ክፍያ ጋር መያያዙ፣ ከኩባንያዎች ተቀናቃኝነት ጋር የተሳሰረ ሊሆን እንደሚችል የሚጠቁሙ መረጃዎች አሉ። ወ/ሮ ታደለች ተመስገን፣ ከሁለት ወራት በፊት ስራ ላይ በአደጋ ህይወቱን ያጣ ሰራተኛ ቤተሰብ ናቸው። የአንድ የአገር ውስጥ ድርጅት ተቀጣሪ የነበረው ሰራተኛ በኢንተርኔት ማስፋፊያ ፕሮጀክት የፋይበር ኦፕቲክስ ዝርጋታ ላይ ነው በአደጋ የሞተው።

የሰራተኛው አሟሟት ላይ ጥያቄዎች ተነስተው እንደነበር የሚታወስ ሲሆን፣ ቀጣሪው ድርጅት በበኩሉ፤ ሰራተኛው አስፈላጊ የጥንቃቄ አልባሳትና መሳሪያዎችን ሲጠቀም እንደነበር በፖሊስ ምርመራ መረጋገጡን ገልጿል። ከሟች ቤተሰብ ጋር በመነጋገር ቀጣሪው ድርጅት የመቶ ሺ ብር ካሳ የከፈለ ሲሆን፣ ፕሮጀክቱን በበላይነት የሚመመራው ሁዋዌ በበኩሉ 200 ሺ ብር ድጋፍ እሰጣለሁ ብሏል። ከዚህ በኋላ ነው፣ ዋንግ ዮንግ ወደ ጅማ መጥቶ “ጋዜጠኛ ነኝ በማለት አጭበርብሯል” የተባለው።

ቻይናዊው ዋንግ ዮንግ መጥቶ እንዳገኛቸውና ሆቴል ድረስ ጠርቶ እንዳነጋገራቸው የጠቀሱት ወ/ሮ ታደለች፣ “ጋዜጠኛ ነኝ፤ ተጨማሪ ገንዘብ እንድታገኙ አደርጋለሁ፤ አዲስ አበባ እንሂድ” በማለት ሊያግባባቸው እንደሞከረ መናገራቸውን ምንጮች ገልፀዋል። ወ/ሮ ታደለች ለፖሊስ ያመለከትኩት ጥርጣሬ ስላደረብኝ ነው ማለታቸው የተገለፀ ሲሆን ፖሊስ በበኩሉ፤ ዋንግ ዮንግ ጋዜጠኛ ሳይሆን የቴሌኮም ኢንጂነርና የዜድቲኢ ሰራተኛ መሆኑን ያረጋገጠው ባለፈው ሳምንት ከሰራተኛና ማህበራዊ ጉዳይ ሚኒስቴር ባገኘው መረጃ ነው ተብሏል። በእነዚህ መረጃዎች የተነሳ፣ ጉዳዩ በዜድቲኢ እና በሁዋዌ መካከል ካለው ተቀናቃኝነት ጋር የተያያዘ ሳይሆን አይቀርም የሚል ጥርጣሬ መፈጠሩ አልቀረም። የዜድቲኢ የህዝብ ግንኙነት ተወካይ ስለ ዋንግ ዮንግ ትናንት ተጠይቀው በሰጡን ምላሽ፣ ዜድቲኢ ለማንኛውም ስራ ወደ ጅማ የላከው ሰራተኛ እንደሌለ እርግጠኞች ነን፤ የሰውዬውን ማንነት አጣርተን እናሳውቃለን ብለዋል።

በ380ሺ ብር ካፒታል ፤ ከመቶሺ በላይ ተሳታፊና እስከ 10ሺ ብር ሽልማት

            በኢትዮጵያ ለመጀመሪያ ጊዜ በአይነቱ ልዩ የሆነ አዲስ የስፖርት ውርርድ ጨዋታ እንደተጀመረ ዳጉ ቤት ኢትዮጵያ ባለፈው ሳምንት በኢንተርኮንትኔንታል ሆቴል ባዘጋጀው ጋዜጣዊ መግለጫ ላይ አስተዋወቀ፡፡ ዳጉ ቤት ኢትዮጵያ በእንግሊዝና ኢትዮጵያ ውስጥ በሚገኙ አራት ኢትዮጵያዊያን የተቋቋመ ድርጅት ሲሆን ለስራው በብሄራዊ ሎተሪ አስተዳደር ሙሉ ፈቃድ አግኝቷል፡፡ የስፖርት ውርርዱ በውጭ ሀገር በሚካሄዱ የስፖርት ውድድሮች ላይ ተመስርቶ የተጀመረ ነው፡፡ በስፖርት የተለያዩ ሁኔታዎች በመወራረድ በህጋዊ መንገድ እየተዝናኑ መጫወት ይቻላል የሚለው ዳጉ ቤት፤ ለሁሉም ባለድርሻ አካላት የገቢ ምንጭ በመፍጠር ለሀገር ጥቅም የሚያስገኝ ስራ እንደሚሆን ተስፋ ያደርጋል፡፡ የስፖርት ውርርዱን በህጋዊ መንገድ መጀመሩ በህብረተሰቡ ዘንድ ህገወጥ በሆነ መንገድ በመወራረድ የሚፈጠሩ አላስፈላጊ ችግሮች እንደሚከላከል የገለፀው ዳጉ ቤት ኢትዮጵያ ከስፖርት ውርርዱ ጋር በተያያዘ በተለያዩ ሁኔታዎች ህብረተሰቡን ተጠቃሚ ለማድረግ እንደሚንቀሳቀስም አስታውቋል።

በዚህም በሀገራችን ለሚገኙ ድጋፍ የሚያስፈልጋቸው የስፖርት ፌዴሬሽኖች እርዳታ በማድረግ ስፖርቱን ለማሳደግ እንደሚሰራ የገለፀው ድርጅቱ በተቋቋመበት የመጀመሪያው አመትም ከተጣራ ገቢው ሃያ በመቶውን ለቦሊንግ አሶሴሽን እርዳታ ለመስጠት መስማማቱንም አመልክቷል፡፡ የዳጉ ቤት ኢትዮጵያ ምክትል ስራ አስኪያጅ አቶ አብርሃም ንጋቱ የስፖርት ውርርዱ መሸነፍ እና ማሸነፍ ያለበት ጨዋታ መሆኑን ሲያስረዱ ተጨዋቾች እና ተሳታፊዎች የስፖርት ውድድሮችን በመመልከት ከሚኖራቸው መዝናናት ባሻገር በሚሰጡት ግምት ተሸላሚ የሚሆኑበትን እድል በመፍጠር እንዲሰራ እና አካሄዱም በህግና ስርዓት የተመራ እንደሚሆን አብራርተዋል፡፡ ዳጉ ቤት ኢትዮጵያን የጀመርነው እንደፓይለት ፕሮጀክት ነው የሚሉት አቶ አብርሃም ንጋቱ፤ የስፖርት ውርርዱን የጀመርነው በለጋሃር አካቢ በሚገኘው ሱቅ እና በድረገፅ በሚደረግ ግንኙነት ነው ብለው ማጫወት የጀመርነው በእግር ኳስ ቢሆንም ወደፊት የቅርጫት ኳስ እና የአትሌቲክስ ውድድሮችንም በማወራረድ ለማጫወት እናስባለን ብለዋል፡፡

በተጨማሪም ወደፊት የውርርዱን መንገድ በአጭር የፅሁፍ መልዕክት እና በሚፋቁ የሎተሪ ካርዶች ለማድረግ እቅድ መኖሩን ተናግረዋል፡፡ የኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌደሬሽንን በመወከል በጋዜጣዊ መግለጫ ላይ ተገኝተው የነበሩት የውድድሮች የስራ ሂደት ባለቤት አቶ ተድላ ዘመናዊ ውርርድ በኢትዮጵያ ስፖርት መጀመሩ እንደሚያስደስት ገልፀው፤ ዳጉ ቤት ኢትዮጵያ ባለድረሻ አካላት ከሆኑት የኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌደሬሽንና የፌደራል ስፖርት ኮሚሽን ግልፅ በሆነ መንገድ ተግባብቶ መስራት እንደሚኖርበት መክረው አወራራጁ ድርጅቱ ስራውን ሲጀምር በውጭ ውድድሮች ላይ ከሚያተኩር ለአገር ውስጥ ውድድሮች ቅድሚያ ቢሰጥ የተሻለ ነበር ብለዋል፡፡ ለነገሩ ዳጉ ቤት ኢትዮጵያ የስፖርት ውርርዱን በውጭ አገር ውድድሮች መጀመሩ የኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌደሬሽን ብቻ ሳይሆን የኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን አሰልጣኝ ሰውነት ቢሻውንና የስፖርት ጋዜጠኞችንም አላስደሰተም፡፡ የብሄራዊ ቡድን ዋና አሰልጣኝ ሰውነት ቢሻው የስፖርት ውርርድ እጅግ አትራፊ ቢዝነስ መሆኑን ተናግረው ዳጉ ቤት ኢትዮጵያ የውርርድ ስርዓቱን በአገር ውስጥ ውድድሮች በተለይ የፕሪሚዬር ሊግ ክለቦችን በማሳተፍ ቢጀመር ምርጫዬ ነበር ካሉ በኋላ ‹‹ውርርድ ካለ የምመርጠው በኢትዮጵያ እግር ኳስ ነበር፡፡

ይህን ለማሳካት ትኩረት ሰጥታችሁ መስራት አለባችሁ፡፡ እግር ኳሱ በተነቃቃ መንፈስ እንዲቀጥል፤ በወጣቶች ላይ በስፋት እንዲሰራ እና ክለቦች የገቢ ምንጮቻቸውን እንዲያሰፉ በሚያደርግ አሰራር ብትንቀሳቀሱ ጥሩ ነው፡፡ ከእነ አርሰናል አስቀድመን ለኢትዮጵያ ክለቦች ማሰብ ይገባል፡፡ የክለቦች መጠናከር ለብሄራዊ ቡድን ድጋፍ እንደሚሆን መታወቅ አለበት፡፡ በማለት ሃሳባቸውን አስረድተዋል። ከጋዜጠኞች መካከልም የዳጉ ቤት ኢትዮጵያ የስፖርት ውርርድ በውጭ አገር ውድድሮች መጀመሩ የአገር ውስጥ ውድድሮች የሚያስፈልጋቸውን ትኩረት ሊያሳጣ አይችልም ወይ በሚል ስጋት የቀረበ ጥያቄም ነበር፡፡ የዳጉ ቤት ኢትዮጵያ ምክትል ስራ አስኪያጅ አቶ አብርሃም ንጋቱ በእነዚህ ሃሳቦች ላይ በሰጡት ምላሽ የስፖርት ውርርዱን በአገር ውስጥ ውድድሮች ለመጀመር የቅርብ ጊዜ እቅድ አለመኖሩን ሲገልፁ በኢትዮጵያ ውስጥ የሚደረጉ የእግር ኳስ ውድድሮች ባላቸው የፉክክር ደረጃ እና ሂደት ለውርርድ በሚያመች ሁኔታ ላይ አለመገኘታቸውን በመጥቀስ የጨዋታዎችን ውጤት በህገወጥ ሁኔታ ለመቀየር የሚያስገድዱ ጥፋቶች በዚህ ምክንያት ሊያጋጥሙ መቻላቸው ሌሎች ችግሮችን ሊያመጣ መቻሉን አስበን የተውነው ነው ሲሉ አብራርተዋል፡፡ በኢትዮጵያ ውስጥ ያሉ የእግር ኳስ ውድድሮች ለስፖርት ውርርድ አመቺ ሊሆኑ እስከሚችሉበት አስተማማኝ የእድገት ደረጃ ግን ድጋፍ በማድረግ አብረን እየሰራን እንቀጥላለን በማለትም ምክትል ስራ አስኪያጁ ቃል ገብተዋል፡፡

በጋዜጣዊው መግለጫ ላይ ተገኝተው የነበሩት የብሄራዊ ሎተሪ አስተዳደር ተወካይ የስፖርት ውርርድን ለማካሄድ የሚያስችል መመርያ በኢትዮጵያ መንግስት የፀደቀው ባለፈው ዓመት መሆኑን ሲገልፁ ፍቃድ የሚያገኙ ድርጅቶች በህግ ማዕቀፍ ሆነው ውርርዱን እንዲያጫውቱ እንደሚደረግና የብሄራዊ ሎተሪ አስተዳደር አፈፃፀሙን በመከታታል በመቆጣጠር አብሮ እንደሚሰራ አስታውቀዋል፡፡ የስፖርት ውርርድ በህጋዊ መንገድ ማከናወን ሊያጋጥሙ የሚችሉ ማህበራዊ ቀውሶችን ለመከላከል አስተዋፅኦ እንዳለው ያስገነዘቡት የብሄራዊ ሎተሪ አስተዳደር ተወካይ ፤ ውርርዱን ለሚያደርግ ተቋም ፈቃድ የምንሰጠው ባለን መመርያ መሰረት ድርጅቱ ከሚያገኘው አጠቃላይ ገቢ የመንግስት 50 በመቶ ድርሻን እንዲከፍል፤ ለማህበራዊ ግልጋሎት ቢያንስ 20 በመቶ ያህል እንዲያበረክት እንዲሁም ውርርዱን ያለምንም ቅሬታዎች እና ችግሮች በትክክል እንዲያከናውን በማሳሰብ ነው ብለዋል፡፡ የትኛውም ድርጅት፤ ተቋም ወይም ግለሰብ ለስፖርት ውርርድ ህጋዊ ፈቃድን ማግኘት እንደሚችል ያስረዱት የብሄራዊ ሎተሪ አስተዳደር ተወካይ ፤ የሚሰጠው ፍቃድ በየዓመቱ የሚታደስ ይሆናል ሲሉ ተናግረዋል፡፡ የስፖርት ውርርድ በዓለም አቀፍ ደረጃ የተስፋፋ ሲሆን ገበያው 70 በመቶ የሚያተኩረው በእግር ኳስ ስፖርት ላይ ነው፡፡ በመላው ዓለም የሚደረጉ የስፖርት አወራራጅ እና አቋማሪ ኩባንያዎችን በመገምገም በየዓመቱ ከ55ሺ በላይ የስፖርት ግጥሚያዎችን የሚከታተለው ስፖርት ራዳር የተባለ ተቋም ይፋ ባደረገው መረጃ ኢንዱስትሪው በየዓመቱ ከ700 ቢሊዮን ዶላር እንደሚንቀሳቀስበት አመልክቷል፡፡

የእንግሊዝ ፕሪሚዬር ሊግ በዓለም አቀፍ አቋማሪ እና አወራራጅ ድርጅቶች ተመራጭ መሆኑን የሚገልፁ መረጃዎች ክለቦች ከ19 የተለያዩ ኩባንያዎች ጋር በአጋርነት በመስራት በዓመት በአማካይ እስከ 6 ሚሊዮን ዶላር እንደሚያገኙ ነው፡፡ በ80 የብሮድካስት ኩባንያዎች ዓለም አቀፍ የስርጭት ሽፋን ያለው የእንግሊዝ ፕሪሚዬር ሊግ ከሚሰሩ አቋማሪ እና አወራራጅ ድርጅቶች በአርሰናል ፓዲ ፓወር፤ በቼልሲና በማንችስተር ሲቲ 188ቤት እንዲሁም በማንችስተር ዩናይትድ ቢዊን በአጋርነት መስራታቸው ይጠቀሳል፡፡ ዳጉ ቤት ኢትዮጵያ የመጀመሪያውን የማጫወቻ ሱቅ ለገሃር ኮሜርስ አካባቢ ከኖክ ማደያ አጠገብ መክፈቱን የገለፁት አቶ አብርሃም ንጋቱ ፤ ዳጉ ቤት ዶት ኮም (www.DagooBet.com) ዌብ ሳይት ኦን ላይን በመጠቀም መጫወት እንደሚቻል አስታውቀዋል፡፡ ውርርዱ የሚካሄድባቸው መንገዶች - አሸናፊውን ቡድን በመገመት መወራረድ - ትክክለኛ ውጤት በመገመት መወራረድ - የጨዋታውን የመጀመሪያ አጋማሸ ውጤት በመገመት መወራረድ - ቀድሞ ጐል የሚያስቆጥረውን ክለብና ተጫዋች በመገመት መወራረድ - የማስጠንቀቂያ ካርድ የሚመለከቱ ተጫዋቾችን በመገመት መወራረድ - እንዲሁም በሌሎች መጫወት ይቻላል ህግጋት እና መመሪያዎች - በ90 ደቂቃ የእግር ኳስ ጨዋታ ውድድር ውጤት መወራረድ ይችላሉ፡፡

- ነገር ግን ውርርዱ የተጨማሪ ሰዓት (30 ደቂቃ) እና የመለያያ ምትን አያጠቃልልም፡፡ - ሁሉም ውርርድ የሚካሄደው ጨዋታው ከመጀመሩ በፊት ይሆናል - 1,X,2 እነዚህ ለውርርዱ የምንጠቀምባቸው ኮዶች ሲሆኑ የሚወክሉልን ጨዋታው ይዞት ሊመጣ የሚችለውን ሦስት አይነት ውጤት ነው፡፡ - 1 ባለሜዳው ያሸንፋል X ቡድኖቹ አቻ ይወጣሉ 2 ከሜዳው ውጪ የሚጫወተው ያሸንፋል፡፡ ስለዚህ በውርርዱ ላይ መሳተፍ የሚፈልግ አንድ ሰው ቢያንስ 3 ጨዋታዎች ቢበዛ ደግሞ 10 ጨዋታዎች ላይ መወራረድ ይችላል፡፡ ለምሳሌ 1 X 2 አርሰናል vs ከማንችስተር 2፡10 3.30 2.90 ሳውዝሃፕተን vs ከፉልሃም 1.80 4.05 3.90 ቶትንሃም vs ኒውካስትል 3.60 3.10 2.75 እርስዎ የመረጡት ከመጀመሪያው ጨዋታ አርሰናል ያሸንፋል ከሆነ ኮድ 1 ሲሆን ያለውም ዋጋ 2.10 ይሆናል በሁለተኛው ጨዋታ ሳውዝሃፕተን ያሸንፋል ብለው መወራረድ ከፈለጉ ኮዱ 2 ሲሆን ያለውም ዋጋ 2.90 ይሆናል ሦስተኛው ጨዋታ በአቻ ውጤት ይጠናቀቃል በለው መወራረድ ከፈለጉ የውርርድ ኮዱ X ሲሆን የውርርድ ዋጋውም 3.10 ይሆናል፡፡ እንበልና ከላይ የመረጡት ሶስቱንም የጨዋታ ውርርድ አሸነፉ፡፡ ከላይ እንደተመለከትነው እያንዳንዱ ውረርድ የራሱ የሆነ ዋጋ አለው ስለዚህ በሶስቱም አሸናፊ ስለሆኑ የሶስቱንም ዋጋ እናበዛለን ይኸውም 2.10 X2.90 X3.10 = 18.87፡፡ መጀመሪያ ላይ ለውረርድ ያስያዙት 10 ብር ቢሆን ከላይ የተመለከተውን የሶስት ጨዋታዎች ዋጋ ብዜትን ማለትም 18.87 ባስያዙት ገንዘብ (10 ብር) በማባዛት የ188.70 አሸናፊ ይሆናሉ፡፡ ነገር ግን ይህ የጨዋታውን ግብር አያጠቃልልም፡፡ ማሳሰቢያ ከተወራረዱ በኋላ የሚሰጥዎትን ደረሰኝ በጥንቃቄ ይያዙ፡፡ አሸናፊ ከሆኑ ደረሰኙን ይዘው በቀረቡ ጊዜ ያሸነፉት ገንዘብ ይከፈልዎታል፡፡

ማራቶን የማዘጋጀት ሃሳብ አላቸው

                በሀዋሳ ከተማ የተገነባውን ገዛኸኝና እልፍነሽ ሆቴልና ሪዞርት ህዳር 14 በይፋ ሲመረቅ ልዩ የ10 ኪሎሜትር የዱላ ቅብብል ውድድር እንደሚካሄድ ታወቀ፡፡ በምረቃው ስነስርዓት ላይ በክብር እንግድነት እንዲገኙ ኡጋንዳዊው የኦሎምፒክ እና የዓለም ሻምፒዮን የማራቶን ድርብ አሸናፊ ስቴፈን ኪፕሮች እና ኬንያዊ አትሌት ጄፈሪ ሙታይ ተጋብዘዋል፡፡ በሌላ ዜና ባልና ሚስቶቹ ማራቶኒስቶች አትሌት ገዛኸኝ አበራ እና አትሌት እልፍነሽ አለሙ በሚቀጥለው ዓመት አንድ የማራቶን ውድድር በኢትዮጵያ ለማዘጋጀት ማሰባቸውን ሲያስታወቁ ተተኪ አትሌቶችን ለማግኘት የአገር ውስጥ ውድድሮች መብዛታቸው አስፈላጊ እንደሆነ ስላመኑበት የነደፉት እቅድ መሆኑን አስረድተዋል፡፡ አትሌት ገዛኸኝ አበራ እና አትሌት እልፍነሽ አለሙ ትናንት በዋና ፅህፈት ቤታቸው በሰጡት መግለጫ የሆቴልና ሪዞርት ምረቃው ከአትሌቲክስ ውድድር ጋር ማያያዝ ያስፈለገው ተተኪ አትሌቶች የእነሱን አርዓያ እንዲከተሉ ለማነሳሳት በማሰባቸው እንደሆነ ተናግረዋል፡፡

አትሌት እልፍነሽ አለሙ‹‹ ማንኛውም ሰው ዓላማዬ ብሎ ከሰራ ለየትኛውም ደረጃ ይደርሳል፡፡ በአሁን ዘመን ያሉ አትሌቶች ደከመን፣ ሰለቸን፤ ከሳን ፤ ጠቆርን ሳይሉ በትጋት መስራት አለባቸው፡፡ በስፖርቱ እኛ የደረስንበት ስኬት ለማግኘት ብቻ ሳይሆን ከእኛ በላይ ውጤታማ መሆን እንደሚችሉ ማወቅ አለባቸው›› ብላለች፡፡ አትሌት ገዛኸኝ በበኩሉ ‹‹እኛ ሮጠን ሆቴሉን ሰርተናል፤ አትሌቱም እንደማንኛውም ህብረተሰብ በትጋት ከሰራ ይሳካለታል፡፡›› በማለት ተናግሯል፡፡ በሆቴልና ሪዞርቱ ምረቃ ላይ የሚካሄደው የ10 ኪሎሜትር የዱላ ቅብብል ውድድሩ መነሻውና መድረሻው ገዛኸኝና እልፍነሽ ሆቴልና ሪዞርት እንደሆነ የገለፀው አትሌት ገዛኸኝ አበራ፤ አንድ ክለብ ሁለት ሴት እና ሁለት ወንድ ባጣመረ የአራት አትሌቶች ቡድን ይወዳደሩበታል ብሏል፡፡

በዱላ ቅብብል ውድድሩ ለመሳተፍ 8 ክለቦች ማረጋገጫ የሰጡ ሲሆን የመከላከያ፤ የማረሚያ፤ የፖሊስ፤ የሙገር እና ሌሎች የሁለተኛ ዲቪዚዮን ክለቦች ተጠቃሾች ናቸው፡፡ አሸናፊ ሊሆን የሚበቃው ቡድን የመጨረሻ ሯጭ የውድድሩ ርቀት ቢያንስ 100 ሜትሮች ሲቀሩት ለገዛኸኝና እልፍነሽ ሆቴልና ሪዞርት ለሚጋበዘው የክብር እንግዳው የምረቃ ሪበኑን እንዲቆርጥ የሚያስረክበበት ሁኔታ መመቻቸቱንም አትሌት ገዛኸኝ አበራ ገልጿል። አንደኛ ለሚጨርስ ቡድን 7ሺ ብር ፤ ለሁለተኛ 5ሺ ብር እንዲሁም ሶስተኛ ለሚወጣው ቡድን 3ሺ ብር ይበረከታል፡፡ ገዛኸኝና እልፍነሽ ሆቴልና ሪዞርት አትሌት ገዛኸኝ አበራ በሲድኒ ኦሎምፒክ በማራቶን አሸንፎ ሲመጣ፣ የደቡብ ክልል መንግሥት በሃዋሳ ከተማ በሸለመው 25ሺህ ካ.ሜ ቦታ ላይ ባለ 5 ኮከብ ደረጃ በመያዝ የተገነባ ነው፡፡ ለሆቴሉ ግንባታ እስካሁን 200 ሚሊዮን ብር ወጭ መደረጉን የገለፀው አትሌት ገዛኸኝ በአሁኑ ጊዜ 150 ሠራተኞች እንዳሉትና የማስፋፊያው ስራ ሲጠናቀቅ ለ500 ሰዎች የስራ እድል እንደሚፈጥር እንጠብቃለን ብሏል፡፡ የገዛኸኝና እልፍነሽ ኢንቨስትመንት በሃዋሳ ከተማ ከሚገኘው ሆቴልና ሪዞርት ብቻ ሳይወሰን በቢሾፍቱ (ደብረዘይት) ከተማም በቢሾፍቱ ሐይቅ ላይ ያሰሩት ባለ 5 ኮከብ ሪዞርት በቀጣዩ ዓመት እንደሚያስመርቁ ፤ በአዲስ አበባም በተለያዩ ቦታዎች የእንግዳ ማረፊያ ሕንፃዎችን እያስገነቡ እንደሆነና በጥቁር ውሃም ቦታ ተረክበው ምን መሥራት እንዳለባቸው እያሰቡ ናቸው፡፡