Administrator

Administrator

               የኢትዮጵያ አየር መንገድ ካዘዛቸው አራት ግዙፍ ቦይንግ 777300ER አውሮፕላኖች የመጀመሪያውን ትናንት የተረከበ ሲሆን፤ ለቦይንግ አውሮፕላኖች የሚያገለግሉ የኤሌክትሪክ መስመሮችን መፈብረክ ይጀምራል ተባለ፡፡ አየር መንገዱ በበረራ ታሪኩ 400 ሰዎች የመያዝ አቅም ያለው አውሮፕላን ሲረከብ የመጀመሪያው ሲሆን፣ አውሮፕላኑ ብዙ መንገደኞችን ለማስተናገድ እንደዋሽንግተን ዲሲ፣ ዱባይና ጉዋንዙ (ቻይና) የመሳሰሉ በተጨማሪ ረዥም ርቀት ያለማቋረጥ መጓዝ እንደሚችል ታውቋል፡፡

በአለም በግዝፈታቸው በሚታወቁና በጄኔራል ኤሌክትሪክ ኩባንያ የተሰሩ ኢንጂነሮች የሚንቀሳቀሰው ይሄው አውሮፕላን፣ በአራት ረዣዥም ክፍሎች በሦስት ረድፍ የተሳፋሪ መቀመጫዎች ሰትሮ የያዘ ነው፡፡ መቀመጫዎቹ ምቹ፣ ቦታው ሰፊና ጣሪያው ከፍ ያለ ነው፡፡ የአውሮፕላኑ አብራሪ ካፒቴን ካሌብ ማሞ፣ ሲያትል ከሚገኘው የቦይንግ ኩባንያ ማዕከል እስከ ቦሌ አውሮፕላን ማረፊያ ለ15 ሰዓታት በመብረር መድረሳቸውን ገልፀው፤ አውሮፕላኑ ዘመናዊ ከመሆኑም በላይ በዘመኑ የቴክኖሎጂ ውጤቶች የተፈበረከ ስለሆነ ለመንገደኞች ከፍተኛ እንደሚሰጥ ተናግረዋል፡፡ የአሜሪካ አምባሳደር ፓትሪሺያ ሃሳላክ በበኩላቸው የቦይንግ እና የኢትዮጵያ አየር መንገድ ግንኙነት ጠንካራ መሆኑን በመጥቀስ፣ አየር መንገዱ ለቦይንግ አውሮፕላኖች የሚያገለግሉ የኤሌክትሪክ መስመሮችን መፈብረክ እንደሚጀምር ተናግረዋል፡፡

ዛሌፍ የሥነ ጥበብ እና ፋሽን ዲዛይን ተቋም፣ በታዋቂ ዲዛይነሮች የተሰሩ አልባሳት የተካተቱበት የፋሽን ትርዒት ዛሬ ከቀኑ 10 ሰዓት በኢንተርኮንቲነንታል ሆቴል እንደሚያቀርብ አስታወቀ፡፡
ከተቋሙ የሥራ ውጤቶች መካከል በ2003 ዓ.ም በአዲስ አበባ ሂልተን የቀረበው በኮንዶም የተሰሩ አልባሳት ዐውደርዕይ ይገኝበታል።

 

Saturday, 02 November 2013 11:54

ወፍ እና ማለዳ

እንኳንስ ችግኙ፣ ሰዎች የተከሉት
ሥር ይይዝ ነበረ፣ አዕዋፍ የዘሩት፡፡
ዘንድሮ ግን ወፎች፣ እንኳንስ ሊዘሩ
ናፍቆኛል ማለዳ፣ መስማት ሲዘምሩ፡፡
ወፎች ከማለዳ
በምን ተቃቃሩ?
ፅልመቱ ሲገፈፍ
እንዳላበሠሩ፤
ማዜም ተስኗቸው
ተዘግቶ ጀንበሩ
ወደሚነጋበት
ወዴትስ በረሩ?!

እችልሻለሁ!!
ስለ እውነት እልሻለሁ፣
ስለወደድኩሽ እችልሻለሁ!
የአያሌ ሞገደኞች ድምር፣ በአንድነት ተጨፍልቆ
ከሰብእናሽ ተላቁጧል፤ አድርጎሻል የሴት ኅልቆ፡፡
ካልተገሩ ባህርያት፣ እስከጠፋ ያለም ፍጥረታት
ነፍስያና አመላቶች ተጎንጉነው ያየሁባት
ብትሆኚም ብቸኛዋ፣ እስከዛሬ ያፈቀርኳት
እልሻለሁ “አያሌዎች”፣ ምስክር ነኝ ስለ እውነት!
ይህም ቢሆን … “እችልሻለሁ!”
ባንዲት ነፍሴ እምላለሁ!
ፍቅር ቀድሞ ገሎኛል፣ ስለምንስ እፈራለሁ?
የምታደርጊውን አድርጊኝ፣ ይኸው ፊትሽ ቆሜያለሁ
(“ሀ-ሞት” ከተሰኘው
የሄኖክ ስጦታው የግጥም መድበል
የተወሰደ - 2005)

                  የመንግሥት ተቋማት አገልግሎት አሰጣጥን በተመለከተ ተደጋጋሚ የነዋሪዎች እሮሮዎችና አቤቱታዎች ሲስተጋቡ የቆዩ ሲሆን መንግስት የአገልግሎት አሰጣጡን ለማቀላጠፍ፣ የስነምግባር ጉድለቶችን ለማሻሻል የተለያዩ እርምጃዎች መውሰዱ ይታወቃል፡፡ ሆኖም ግን አሁንም ችግሮቹ እንዳልተፈቱ ብዙዎች ይናገራሉ፡፡ ባለፈው ሰሞን የማህበራዊ ጥናት መድረክ “የህዝብ አገልግሎት አሰጣጥ ስነምግባርና ተጠያቂነት” በሚል ርዕስ በግዮን ሆቴል ዎርክሾፕ አዘጋጅቶ ነበር፡፡ በዎርክሾፑ ላይም የቀድሞ ሲቪል ሰርቪስ ኮሚሽነርና አሁን በግል አማካሪነት የሚሰሩት አቶ አትክልት አሰፋ እና የቀድሞ ሲቪል ሰርቪስ ጀነራል ዳይሬክተርና አሁን በግል ስራ ላይ የተሰማሩት የህግ ባለሙያ አቶ መስፍን ታፈሰ እንዲሁም የማህበራዊ ጥናት መድረክ ስራ አስፈፃሚ ዳይሬክተር፣ ዶክተር ምህረት አየነው የቀረበውን ፅሁፍ የሚተች ዳሰሳ አቅርበዋል፡፡
ኢትዮጵያ አስራ አራት የመንግሥት አገልግሎት ማሻሻያ ፕሮግራም እንዳላትና ሁሉም ፕሮግራሞች አገር በቀል እንደሆኑ የገለፁት አቶ አትክልት አሰፋ፤ ዋናው ፕሮግራም የመንግስት አገልግሎት (ሲቪል ሰርቪስ) ማሻሻያ እንደሆነ አስረድተዋል። በአገልግሎት አሰጣጥ ላይ ለውጥ ለማምጣት የሚያስችሉ ተቋማት መቋቋማቸውን፤ የተለያዩ የህግ ማእቀፎችም መዘጋጀታቸውን አቶ አትክልት ጠቁመዋል፡፡ ችግሮች ቢኖሩም ትልቅ ለውጥ መታየቱን የተናገሩት አቶ አትክልት፤ የሙስናውም ደረጃ በንፅፅር ሲታይ በዝቅተኛ ደረጃ ላይ መሆኑን ጠቁመው፤ በተለያዩ የአገልግሎት ዘርፎች የሚስተዋሉ የስነምግባር ጉድለቶች እና ግድፈቶችን ዘርዝረዋል፡፡
በመጀመሪያ የተዳሰሰው የትምህርት ዘርፍ ሲሆን በፈተና እና በውጤት አሰጣጥ ላይ የሚፈፀሙ ማጭበርበሮች፣ ጉቦ መቀበል፣ የሀሰት ትራንስክሪፕትና ሰርተፊኬት መስጠት፣ የመምህራንን እድገት እና ዝውውር ከጥቅም ጋር ማያያዝ፣ ሴት ተማሪዎችን ለወሲብ ማስገደድና የመምህራን ለግል ስራ ቅድሚያ መስጠት እንዲሁም በስራ ገበታ ላይ አለመገኘት የሥነምግባር ጉድለቶች ተብለው ተጠቅሰዋል፡፡ በጤና ዘርፍ ደግሞ ለኤክስሬይ እና ለቀዶ ጥገና አገልግሎቶች ጉቦ መጠየቅ፣ የሆስፒታል አልጋ በጉቦ ወይም በዝምድና እንዲሰጥ ማድረግ፣ ለታካሚዎች ተገቢውን እንክብካቤ ያለማድረግ፣ የባለሙያ የብቃት ማነስ፣ የመድሀኒት እና የአምቡላንስ አቅርቦት ያለመኖር፣ አላስፈላጊ ምርመራዎችን በማዘዝ ታካሚዎችን ላላአስፈላጊ ወጪ መዳረግ፣ ታካሚዎችን ወደ ግል ፋርማሲ እና ክሊኒኮች መላክ፣ ተቆጣጣሪን በጉቦ መደለል እና የማጭበርበር ድርጊት መፈፀም፣ መገልገያ ቁሳቁሶችን መስረቅ እና ፈንድ ያለ አግባብ መጠቀም እንደ ጉድለት ቀርበዋል፡፡
አቶ አትክልት፤ ፍርድ ቤቶች፣ አቃቤ ህጎችና ፖሊስ ዘንድ ይፈፀማሉ ያሏቸውን የስነምግባር ጉድለቶችም በዳሰሳቸው ዘርዝረዋል፡፡ ከእነዚህም መካከል፡- ፍርድ ቤቶች እና አቃቤ ህጎች ውሳኔን ለማስቀረት ወይም ለመጀመር ጉቦ መጠየቅ ወይም መቀበል፣ የአቃቤ ህጎች ስልጣናቸውን በመጠቀም ክሶችን መግደል ወይም ነፍስ እንዲዘሩ ማድረግ፣ ክስን በአግባቡ ያለመያዝና በፍትህ አስተዳደሩ ላይ የሚታዩ መጓተቶች፣ የብቃት ማነስ እና ጉቦ በመቀበል ክስን ማቅለል… የሚሉት ይገኙባቸዋል። የፖሊሶችን የስነ ምግባር ጉድለቶች ሲጠቅሱም፤ እስረኞችን በአግባቡ ያለመያዝ፣ የትራፊክ ፖሊሶች ህገወጥ ሾፌሮችን በጉቦ ማሳለፍ እንዲሁም በፀጥታ ጥበቃ ላይ የተሰማሩ ፖሊሶች በጥፋት መጠየቅ ያለባቸውን በጥቅም በመደለል አለመጠየቅ፣ ማስረጃዎችን ለማድበስበስ ምስክሮችን እንዳይቀርቡ ማድረግ… የሚሉትን ዘርዝረዋል፡፡
በንግድና ኢንቨስትመንት ከሚስተዋሉ የስነምግባር ጉድለቶች ውስጥም ህገወጥ ፈቃድ መስጠት፤ በህገ ወጥ፣ ደረጃቸውን ባልጠበቁና ጥራታቸው በተጓደለ ምርቶች ላይ የሚደረግ ክትትልና ቁጥጥር የይስሙላ መሆን፣ የሸቀጦች እጥረት ላይ የሚደረግ ቁጥጥር ማነስ የተጋነነ የዋጋ ማሻቀብ እና የውድድር መንፈስን በሚቃረኑ እና ከእውነት በራቁ የሸቀጦች ማስታወቂያ ላይ የሚደረጉ ቁጥጥሮች ማነስ በጥናቱ ላይ ተጠቅሰዋል፡፡
ከመሬት ጋር በተያያዘ የሚፈፀሙ የስነምግባር ጉድለቶችን በተመለከተ ደግሞ በቤት ልማት ላይ የተሰማሩ ባለሀብቶችን በቦታ አሰጣጥ ላይ በእኩል አይን አለማየት፣ የተጭበረበሩ የመሬት ባለቤትነት ሰርተፊኬትና ሰነድ አዘጋጅቶ መስጠት የሚሉት በዋናነት የስነምግባር ጉድለቶች ተብለው ተቀምጠዋል፡፡
የመንግስት ቤቶችን አስመልክቶም፤ ቤት ያለጨረታ ማከራየት፣ በኪራይ አሰባሰብ ላይ የብቃት ማነስና መዘግየት፣ በህገወጥ መንገድ ቤት በያዙና በተከራይ አከራይ ጉዳይ ላይ የክትትል ማነስ፣ ከህግና ደንብ ውጭ መስራት፣ በኪራይ ተመን ላይ ወጥ ያለመሆን እና የተቀናጀ የመረጃ ዘዴ ያለመኖር… የተጠቀሱ ሲሆን፤ በአገልግሎት ዘርፍም የእቃ ግዢና አቅርቦት ችግር፣ ተደጋጋሚ የመብራት እና የውሀ መጥፋት፣ የዘገየ የስልክ ጥገና እና ቀርፋፋ የኢንተርኔት አገልግሎት ጉድለት ተብለው ተዘርዝረዋል፡፡
የኮንስትራክሽን ዘርፉም ከስነምግባር ጉድለቶች አላመለጠም - በአቶ አትክልት ዳሰሳ መሰረት፡፡ ግንባታዎችን ማጓተት፣ ጥራቱን ያልጠበቀ ግንባታ መቀበል፣ የዋጋ መዛባት፣ በኮንትራክተሮች እና በሱፐርቫይዘሮች መካከል የሚደረግ መመሳጠር፣ ላልቀረቡ እቃዎች ክፍያ መፈፀም፣ ብክነት፣ ስርቆት እና አግባብ ባልሆነ መንገድ ተጫራቾችን መለየት የሚሉ ይገኙበታል፡፡
የቤቶች ልማት ፕሮጀክት ላይ የሚታዩ የሥነምግባር ጉድለቶችን የዳሰሱት አቶ አትክልት፤ ህግን ባልተከተለ መንገድ ያለ እጣ ለነዋሪዎች ቤት መስጠት፣ ባልና ሚስትን የሁለት ቤቶች እድል ተጠቃሚ ማድረግ፣ የከተማዋ ነዋሪ ያልሆኑና ያልተመዘገቡ ሰዎችን ተጠቃሚ ማድረግ እና በርክክብ ላይ የሚታይ መዘግየትን ጠቅሰዋል፡፡ ለቀበሌ እና የወረዳ ተመራጮች
የሚሰጣቸው የቅድሚያ የቤት እድል፣ ብቃት የሌላቸውን ሰዎች ለስራ መመልመል፣ የነዋሪነት የቀበሌ መታወቂያና ሰርተፊኬት በጉቦ መስጠት፣ የገንዘብ ብክነት፣ በህገወጥ የቤቶች ግንባታ ላይ ወቅታዊ ቁጥጥር እና እርምጃ ያለመውሰድ እንዲሁም በስብሰባዎች መብዛት ሳቢያ የጊዜ አጠቃቀም ላይ የሚፈጠሩ ችግሮች ተዘርዝረዋል፡፡
ቀደም ሲል በብቃቱና በቅልጥፍናው የሚታወቀው ኢሚግሬሽን፤ በአሁኑ ወቅት ፓስፖርት ለመስጠት ረጅም ጊዜ እንደሚወስድበት የተጠቀሰ ሲሆን መንግስታዊ ባልሆኑ ድርጅቶችና በሲቪል ማህበራት ላይ ጠበቅ ያለ ቁጥጥር እንደማይደረግም አቶ አትክልት በጥናታቸው ገልፀዋል፡፡
በጥናቱ ላይ ትችት ያቀረቡት አቶ መስፍን በበኩላቸው፤ የስነምግባርና የአገልግሎት አሰጣጥ ማሻሻያ ፕሮግራሙ ዲዛይን ከጊዜ ጋር የመራመድ ሁኔታው ምን ይመስላል? ትግበራውስ ምን አይነት ቅደምተከተል የያዘ ነው? በማሻሻያ ፕሮግራሙ ላይ የሰው ሀይሉ ሚና ምን ይመስላል? ቢፒአር ምን ያህል ከፖለቲካ የፀዳ ነው? ውጤታማ ነው ሲባል ውጤቱ እንዴት ይለካል? የሚሉ ጥያቄ አዘል ትችቶችን ሰንዝረዋል፡፡
ዶክተር ምህረት ደግሞ ትኩረት ያደረጉት በጥናታዊ ፅሁፉ ጎልተው መውጣት አለባቸው ባሏቸው ነጥቦች ላይ ነው፡፡ በመንግስት አገልግሎት አሰጣጥ ስነምግባር እንዲሰፍንና ተጠያቂነት እንዲጎለብት በሙያው የዳበረ፣ ነፃና በችሎታው ብቻ የተመረጠ የመንግስት ሠራተኛ ወሳኝ ነው ብለዋል። “ሰራተኛው ከፓርቲ ወይም ከፖለቲካው ቁጥጥር ነፃ ሆኖ በሙያው የተካነና ለሀላፊነቱ ተጠያቂ ቢሆን አብይ መስፈርት ነው ብዬ አስባለሁ” ብለዋል፡፡ “የስነ ምግባር ወይም የአፈፃፀም ጉድለቱን በፓርቲ ጥላ ስር መደበቅ ያለበት አይመስለኝም፡፡ በሙያው ይፈረጃል፤ ይመለመላል፣ ያድጋል፣ ይደራጃል፡፡” ሲሉም አብራርተዋል፡፡
ነፃ የሆነና በሙያው የተካነ ጋዜጠኛና ሚዲያ መኖር ዋነኛ የፖሊሲ ጥያቄ እንደሆነም ዶ/ር ምህረት ተናግረዋል፡፡ ተንቀሳቅሶ ማንቀሳቀስ የሚችል ሲቪል ማህበረሰብ ያስፈልጋል፤ ይሄ ጎላ ብሎ መውጣት አለበት ያሉት ዶ/ሩ፤ ነፃና ጠንካራ የሙያ ማህበራት ያስፈልጋሉ ብለዋል፡፡ “ዎች ዶግ” ተቋማት ነፃ ሆነው በህግ መሰረት መጠናከር እንዳለባቸውም ገልፀዋል። “ማሻሻያው” ብዙ ነው፤ የአንዱ ጥቅምና ጉዳት ሳይታይ በላዩ ላይ መደረብ ጉዳት አለው” ብለዋል - ዶ/ር ምህረት ባቀረቡት ጥናት፡፡

አንድ አዋቂና አስተዋይ የተባ ለመምህር ተከታዮቹን ይዞ ረዥም መንገድ ይሄድ ነበር ይባላል፡፡ በመንገዳቸው ላይ አንዲት የታሠረች ጥቁር ላም ይመለከታል፡፡ ከዚያም ወደ ተከታዮቹ ዞሮ፤
“የዚችን ጥቁር ላም ወተት መጠጣት ውጉዝ ነው!” አለ፡፡
ተከታዮቹ በአንክሮ አዳመጡት፡፡ መንገዳቸውን ቀጠሉ፡፡ ወደ አንድ መንደር ሲደርሱ፤ እኔ እዚህ አድሬ አረፍ ልበል፤ እናንተ ደግሞ ወደየመንደሮቻችሁ ተጠግታችሁ እደሩና ጠዋት ከዚሁ መንገድ እንቀጥላለን አላቸው”
ሁሉም ወደሚያድሩበት ሄዱ፡፡
በየደረሱበት ግን ለሰው ትምህርት ለመስጠት ሞከሩ፡-
“የጥቁር ላም ወተት ውጉዝ ነው እነዳትጠጡ” እያሉ አስተማሩ፡፡
ህዝቡም
“ይህንን ማን አለ?” ሲል ጠየቀ፡፡
“መምህራችን!” አሉት፡፡
ጥቁር ላም ያለው ሰው ሁሉ ከፊሉ አዘነ፡፡ ከፊሉ ግራ ተጋባ፡፡ ከፊሉ “መምህርን መጠየቅ አለብን፡፡ አንድ ደሀ ሰው ያለችው አንዲት ጥቁር ላም ብቻ ብትሆንስ? በምኑ ይኖራል?” ሲል አጉረመረመ፡፡
በነጋታው መምህሩ በመንደራቸው ሲያልፍ፣ “መምህር ሆይ የጥቁር ላም ወተት መጠጣት
ስለምን ተከለከለ፣ ስለምንስ ውጉዝ ነው አልክ?” ሲሉ ጠየቁት፡፡
መምህሩም፤
“ተከታዮቼ የጥቁር ላም ወተት መጠጣት የተወገዘ ነው” ብለዋችሁ ከሆነ ተሳስተዋል፡፡ እኔ ያልኩት ነገር የሚመለከተው፣ ትላንት መንገድ ላይ ያየናትን ጥቁር ላም ነው” አላቸው፡፡
ሰዎቹም “ያቺንስ ጥቁር ላም ምን የተለየ ነገር ብታይባት ነው? አሉና ደግመው ጠየቁት፡፡
“መልካም ጥያቄ ነው፡፡ ተከታዮቼም ይህን ጥያቄ ሊጠይቁኝ ይገባ ነበር፡፡ ያቺ ጥቁር ላም እበረት ውስጥ ታስራለች፡፡ ምንም ምግብ አይሰጥዋትም፡፡ ሆኖም ጠዋት ማታ ያልቧታል፡፡ ይሄ ተግባር ግፍ ነው፡፡ ወተቱም ከግፍ የተገኘ ወተት ይሆናል፡፡ ውጉዝ ነው ያልኩት ለዚህ ነው፡፡ የጥቁርዋ ላም ምሳሌነቱ በግፍ ለተገኘ ማናቸውም ገንዘብ ንብረትና ሀብት ሁሉ ነው!” ሲል አብራራላቸው፡፡
* * *
ነገርን በጅምላው መውሰድ ስህተት ላይ ይጥለናል፡፡ የዓለምን ተመራማሪዎች ሲያጣሉና ተከታዮችንም ሲያወዛግቡ የኖሩ አያሌ ጥያቄዎች ከትርጓሜ ስህተት የመጡ እንደሆኑ አንዘንጋ፡፡ በእኩይ መንገድ የተገኘ ማናቸውም ዓይነት ብልፅግና ያስጠይቃል ፡፡ ሊያስጠይቅ የሚችልን ማናቸውም ኢፍትሐዊ ነገር የፈፀመን አለቃም ሆነ ምንዝር፤ ባለሥልጣንም ሆነ ተከታይ ጉዳዩን አብራርቶ እንዲጠይቅ ማድረግ የተበዳይ መብት ነው፡፡ ላሚቱ ራሷም ተዟዙራ የምትበላው እንዳትፈልግ አስረን ስናበቃ ያልሰጠነውን ለመቀበል፣ ያልመገብነውን ለማለብ መፈለግ፣ የሚገኘውን ወተት የግፍ ንብረት እንደሚያደርገው ማስተዋል ዋና ጉዳይ ነው፡፡ የበታቾቻችን፣ ተከታዮቻችን፣ ካድሬዎቻችን በየደረጃው ለመርሆች፣ ለመመሪያዎችና ለራዕዮች የሚሰጡት ትርጓሜ የተሳሳተ ከሆነ፤ የሚሳሳተው ብሎም የሚጎዳው፣ አገር ሙሉ ሰው ነው፡፡ ስህተቱ እጅግ የከፋ የሚሆነው ደግሞ የሚሰጠውን መግለጫ ህዝብ አብራሩልኝ ሲል “እኔ ያልኩህን ብቻ ተቀበል” የምንል ከሆነ ነው፡፡ አንድም ያለዕውቀት አንድም በዕብሪት፣ ይህን ግትርነት ካሳየን አስከፊ ጥፋት ከመሆን አይዘልም፡፡ የመንግሥት ሠራተኛም ቢሆን የህዝብ አገልጋል እንጂ ገዢ ነኝ የሚል አስተሳሰብ ካለም አደገኛ ነው! አገርና ህዝብን መበደል ነው፡፡ ዋና ዋና መርሆቻችንና የፖለቲካ አቋሞቻችንን ከመመርመርና ቆም ብለን ከማየት ይልቅ በደመ-ነብስ መከተልና እንደቦይ ውሃ አብሮ መፍሰስ ከዚያም ይልቅ የበለጠ መጮህ፤ ቢያንስ የዋህነት ነው፡፡
አሌክሳንደር ፓፕ የተባለው ገጣሚ “በጭፍኑ መስማማት መዋሸት ነው” ይለናል /To blindly comply, is to lie/፡፡
በሀገራችን ተጠይቀው ያልተመለሱ፤ ተመልሰው ያላጠገቡ፤ ከናካቴው ያልተጠየቁ ወይም ለመጠየቅ የሚፈሩ፤ በርካታ የፖለቲካም፣ የኢኮኖሚም፣ የማህበራዊም፣ የባህልም ጥያቄዎች በልማድ ታጅለው ብዙ ጊዜ አልፏቸዋል፡፡ አንዳንዶቹ፤ ብንጠይቅ ማን ይመልስልናል በሚል ሰበብ፣ እንደተዳፈኑ የሚቀሩ ናቸው፡፡ አንዳንዶቹ ብንጠይቅ እንጠየቃለን በሚል ፍርሃት የሚዳፈኑ ናቸው፡፡ ጥቂቶቹ መጠየቅ እንዳለባቸው ሳናውቅ እንደቀለጡ የሚቀሩ ናቸው፡፡ አብዛኞቹ በምን ያገባኛልና በምን-ግዴ፣ ቸልታ የተሸፋፈኑ ናቸው፡፡ ዞሮ ዞሮ ሁሉም ጉዳት ሲያደርሱብን ማየታችን አልቀረም፡፡ በተናጠል የምናብጠለጥላቸውና የምንሸሙርባቸው፤ እንዲሁም በንቀት የምናንጓጥጥባቸው ግን፤ ሲደርሱብን እሪ የምንልባቸው፤ በርካታ የዕለት-ጉርስ የዓመት-ልብስ ተኮር አንገብጋቢ ጥያቄዎች እንደ ዐባይ ከዓመት ዓመት ይፈስሳሉ፡፡
“ከበሮ የተደለቀውን ያህል ይጮሃል” የሚለው ተረት፤ የመቺውን እንጂ የተመቺውን ድምፅ የማያስተጋባበት ሁኔታ ውስጥ ከሆነ ያለነው፣ የትርጓሜ ስህተት አለ ማለት ነው፡፡ ያ ደግሞ የጥቁሯን ላም ያህል አሳሳቢ ችግር ሆኖ እናገኘዋለን፡፡ የበደሉንን ይቅር ማለት ብቻ ሳይሆን መጠየቅም መልካም ሥነ-ምግባር ነው! የከበሮ መቺውንም፣ የተመቺውን ከበሮም፣ ነገር ለማወቅ የጠያቂነት ባህል እናዳብር!!

ሃዋሣ ከተማ ላይ የተካሄደው 1ኛው ኃይሌ ገ/ስላሴ ስኬታማ አጀማር እንደነበረው ተገለፀ፡፡ ባለፉት አራት ዓመታት በሃዋሣ የግማሽ ማራቶንና የጎዳና ላይ ሩጫዎችን ያካሄደው ታላቁ ሩጫ በኢትዮጵያ የመጀመሪያ የማራቶኑን በአስደናቂ ዝግጅት በማካሄድ ዓለም አቀፍ ደረጃ ያለው የአትሌቲክስ ውድድሮች አዘጋጅ ተብሏል፡፡ የኢትዮጵያ አትሌቲክስ ፌደሬሽን ከሚያካሂዳቸው የሞሃ ማራቶን እና የአበበ ቢቂላ ማራቶን ነበሩ፡፡ በግል ተቋም በታሪክ የመጀመርያው የማራቶን ውድድር አንደኛው የኃይሌ ገብረስላሴ ማራቶን” ነው፡፡ ማራቶኑ በሌሎች የታላቁ ሩጫ በኢትዮጵያ ውድድሮች ታጅቦ የተካሄደ ሲሆን የህፃናት የ2ኪ.ሜ የጐዳና ውድድር፣ የ5 ኪ.ሜ ህዝብ አሳታፊ ሩጫ እና የግማሽ ማራቶን ውድድሮች ናቸው፡፡ የኃይሌ ገ/ስላሴ ማራቶን በሃዋሣ ከተማ አውራ ጐዳናዎች የተደረገው በተገቢው የማራቶን ርቀት ሲሆን በአይ. ኤ. ኤ. ኤ ፍ ባለሙያ ሂውጅ ጆንስ በሰራው ልኬት ማረጋገጫ እና ዕውቅና አግኝቶ ነው፡፡
ማራቶኑን በማዘጋጀት በተለይ ሶስት አካላት በአጋርነት ሰርተዋል፡፡ በማርኬቲንግ እና በፕሮሞሽን እንቅስቃሴዎች በባለቤትነት የመራው የአሜሪካው ሞራይ ማውንተን ስፖርትስ ነው፡፡ ታላቁ ሩጫ በኢትዮጵያ የውድድሩን ዝግጅት እና ኦፕሬሽን አከናውኗል፡፡ አዋዜ ቱርስ ደግሞ ከውድድሩ ጋር በተያያዘ በተለይ የውጭ አገር ተሳታፊዎች በማቀላጠፍ ተሳትፏል፡፡ ኃይሌ ገ/ስላሴ ማራቶንን የማዘጋጀት ሃሳብን የተወጠነው በአሜሪካው የአትሌቲክስ ውድድሮች አዘጋጅነት በሚታወቀው ሞራይ ማውንቴን ስፖርትስ ነበር፡፡ የሮክን ሮል ማራቶን እና ታዋቂውን የግራንድ ፕሪ ውድድር ካርልስባድ የማዘጋጀት ልምድ አለው
የታላቁ ሩጫ በኢትዮጵያ ስራ አስኪያጅ አቶ ኤርሚያስ አየለ እንደገለፀው ሞራይ ማውንቴን ስፖርትስ ሃሳቡን ያመነጨው በአሜሪካ እና በአውሮፓ ከሚካሄዱ ውድድሮች የተለየ ማራቶን መዘጋጀት አለበት በሚል ነው፡፡ ስለዚህም ታላላቅ የረጅም ርቀት ሯጮችን በማፍራት ወደ የሚታወቁት ሁለቱ የምስራቅ አፍሪካ አገራት ኬንያና ኢትዮጵያ ተተኮረባቸው። ከኃይሌ ገብረስላሴ ጋር በነበራቸው ትውውቅ ኢትዮጵያ ተመረጠች፡፡
ሞራይ ማውንቴን ስፖርትስ ለታላቁ ሩጫ በኢትዮጵያ ዝግጅት ክፍያ በመፈፀም ፤ለውድድሩ የሚያስፈልገውን ወጭን በመበጀት፤ ስፖንሰሮችና ባለ ድርሻ አካላትን በማስተባበር፤ የውጭ ተሳታፊዎችን በመማረክ እና አጠቃላይ የማስተዋወቅ እና የፕሮሞሽን ተግባራትን በዋና አጋርነት ሰርቷል፡፡ አቶ ኤርሚያስ አየለ እንደገለፀው የኃይሌ ገብረስላሴ ማራቶንን ለማሰናዳት በውድድሩ ዙርያ የተሰባሰቡ አጋሮች ለአንድ አመት ሰርተዋል፡፡ ሞራይ ማውንቴን ስፖርትስ አማካኝነት ስለየኃይሌ ገብረስላሴ ማራቶንን በታላላቆቹ የኒውዮርክ፤ ቺካጎ እና የበርሊን ማራቶኖች በክፍያ በሚገኝ ቦታ ቢልቦርዶችን በመስቀል ማስተዋወቅ ተደርጓል፡፡ ሞራይ ማውንቴን ስፖርትስ የዚህን ውድድር አጠቃላይ ወጪ የሸፈነ ሲሆን እስከ 2 ሚሊዮን ብር ወጭ አድርጓል፡፡ ይህንኑ ማራቶንን ምክንያት በማድረግ በተዘጋጀ የገቢ ማሰባሰቢያ እንቅስቃሴ 200ሺ ዶላር ማግኘት ተችሏል፡፡ ይህ የገንዘብ ድጋፍ ሙሉ ለሙሉ በሞራይ ስፖርትስ አማካኝነት የተገኘው የገንዘብ ድጋፍ ከልብ ጋር በተያያዘ የጤና ችግር ድጋፍ ለሚሹ እና ለተቸገሩ ህፃናት እርዳታ ለሚሰጠው ለእንጦጦ ፋውንዴሽን የተበረከተ ነው። የሃዋሳው ውድድር የዓለም ማራቶን ሪከርድ ለሁለት ጊዜያት በሰበረው ታላቁ የማራቶን ሯጭ ኃይሌ ገ/ስላሴ በመሰየሙ በርካታ የውጭ አገር ስፖርተኞች ወደ ኢትዮጵያ መጥተው ውድድሩ ላይ እንዲሳተፉ ምክንያት ነበር፡፡ ለማራቶኑ ድረገፅ ከፍተኛ ዓለም አቀፍ ትኩረትም የጠቀመ አሰያየምም ነው፡፡
ታላቁ ሩጫ በኢትዮጵያ ላለፉት 4 ዓመታት በሃዋሣ ከተማ የ5 ኪሎ ሜትር የጎዳና ላይ ሩጫዎች የግማሽ ማራቶን ውድድሮችን ሲያዘጋጅ ቆይቷል፡፡ ይህ ልምዱ በኃይሌ ገብረስላሴ ማራቶን ዝግጅት የተቀላጠፉ ስራዎች እንዲከናወኑ አግዟል፡፡ በሐዋሳ ከተማ ለውድድሩ የተመረጡት አውራ ጎዳናዎች ሜዳማ መሆናቸውና አቀበትና ቁልቁለት ስላልበዛባቸው ለአትሌቶች የተመቹ ነበሩ፡፡ የአየሩ ሁኔታ ግን በሙቀት ሳቢያ ትንሽ አስቸጋሪ ስለነበር የውድድሩ አዘጋጆች ማራቶኑ በማለዳ እንዲካሄድ አድርገዋል፡፡ የማራቶን ውድድሩ በተሳካ ሁኔታ ተዘጋጅቶ፣ በአማረ ሁኔታ ተስተናግዶ እና በሰለማዊና በአስደናቂ የውድድር መንፈስ ታጅቦ መጠናቀቁን አቶ ኤርምያስ አየለ ይገልፃል፡፡ ስኬታማ አጀማመር እንዳደረግን ያረጋገጥነው ሐዋሣ ከተማ ለማራቶን የምትመች መሆኗን ስላመለከትን በርካታ ተሳታፊዎች ከውጭ መጥተው በመወዳደራቸው፤ ሁሉም ተሳታፊዎች በማራቶኑ የተሰማቸውን እርካታ በ99 በመቶ በመግለፃቸው፤ የማራቶን ርቀቱን በ7 ሰዓት ጨርሶ የገባ ተወዳዳሪ እንኳን ሩጫውን በከፍተኛ ሁኔታ እንደተደሰተበት ማሳወቁ እንዲሁም በአጠቃላይ ክንውኑ ስፖርትና ቱሪዝምን በማስተሳሰር በታየበት ውጤት እንደነበርም አብራርቷል፡፡
በኃይሌ ገብረስላሴ ማራቶን እና በ5ኪሎሜትር የጎዳና ላይ ሩጫው እና በግማሽ ማራቶን ውድድር ለመሳተፍ ከውጭ አገር የመጡ ስፖርተኞች ብዛት እስከ 150 መድረሳቸው መሆኑ ለውድድሩ ጥሩ አጀማመር መገለጫ የሚሆን ነው የታላቁ ሩጫ በኢትዮጵያ ስራ አስኪያጅ አቶ ኤርሚያስ አየለ፤ ከእነዚህ የውጭ አገር ተሳታፊዎች 50ዎቹ በማራቶን እንዲሁም 32 ያህል በግማሽ ማራቶን በመወዳደር ደስተኞች ናቸው ብሏል። የማራቶን ውድድሩ ከተዘጋጀባቸው አላማዎች ዋንኛው ለአገር ውስጥ አትሌቶች የውድድር እድል ለመፍጠር ነው፤ በውድድሩ ላይ ከ40 በላይ ክለቦች አትሌቶቻቸውን አሳትፈዋል፤ የግል ተወዳዳሪዎች ምቹ መስፈርት በማውጣት እንዲካፈሉ ተደረጓል ማራኪ የገንዘብ ሽልማት በማቅረብም ለውድድሩ ትኩረት ተፈጥራል፡፡ በውድድሩ ለሚሳተፉ አትሌቶች በሁለቱም ፆታዎች በሽልማት እና በስጦታ እስከ ግማሽ ሚሊዮን ብር መሰጠቱን የገለፀው አቶ ኤርሚያስ፤ በወንዶች የማራቶን ርቀቱን ከ2 ሰዓት 12 ደቂቃ በታች ለሚገባ 100ሺ ብር እንዲሁም በሴቶች 2 ሰዓት ከ30 ደቂቃ በታች ለምትገባ 100ሺ ብር የቦነስ ሽልማት ቀርቦ ነበር ብሏል፡፡ በውድድሩ ላይ ያሸነፉ አትሌቶች አዘጋጆቹ ምርጥ ሰዓት ያላቸውን አትሌቶች አብዝተው ቢያሳትፉ እና አሯሯጮችን ቢመድቡ የተሻለ ነበር በማለት ለስፖርት አድማስ አስተያየት ሰጥተዋል፡፡ በሌላው የዓለም ክፍል አትሌቶችን ለተሳትፎ በመክፈል እና የሚከፈላቸውን አሯሯጮች በመቅጠር ይሰራል። በኃይሌ ገ/ስላሴ ማራቶን በዚህ መንገድ የመስራት እቅድ ያልበረን ኢትዮጵያ የሯጮች አገር እንደመሆኗ ጥሩ ተወዳዳሪ ማግኘት ስለማንቸገር ነው ያለው አቶ ኤርሚያስ፤ በዚህ ውድድር ላይ ተሳትፈው እስከ 30ኛ ደረጃ የሚያገኙ አትሌቶች በሌላው አለም ጥሩ የማራቶን ተወዳዳሪ ሊሆኑ መቻላቸውን መታሰብ እንዳለበት ያስገነዝባል፡፡
የመጀመርያው አሸናፊ መሆኔ ትልቅ ታሪክ ነው
አትሌት ጉዲሳ ሸንተማ
ባለፈው ሰሞን አንደኛውን የኃይሌ ገ/ስላሴ ማራቶን ከማሸነፉ በፊት አትሌት ጉዲሣ ሸንተማ በትልልቅ የማራቶን ውድድሮች ሰፊ ዓለም አቀፍ ልምድም ነበረው፡፡ በ2006 እ.ኤአ በበርሊን ማራቶን ኃይሌለ ተከትሎ በመግባት በ2ኛ ደረጃ ሲያጠናቅቅ ርቀቱን በ2 ሰዓት ከ10 ደቂቃ ከ47 ሰከንዶች በሆነ ጊዜ በመሸፈን ነበር፡፡ በ2008 እ.ኤ.አ ላይ ደግሞ በፓሪስ ማራቶንና፣ በዱባይ ማራቶን ተወዳድሮ በተመሳሳይ 4ኛ ደረጃን አግኝቷል፡፡ ማራቶኑን በጥሩ ሁኔታ በመቆጣጠር ተወዳድርያለሁ ብሎ ለስፖርት አድማስ የተናገረው አትሌት ጉዲሣ ሸንተማ የኃይሌ ገ/ስለሴ ማራቶንን የመጀመርያው አሸናፊ መሆኔ ትልቅ ታሪክ ነው ሲል ተሳትፎውን ለሽልማት በመጓተት ሳይሆን፣ በኃይሌ መሰየሙንና እንደተምሳሌት ስለሚመለከተው በከፍተኛ ደስታ ተቀብሎታል፡፡ የመሮጫ ጐዳናው ዳገትና ቁልቁለት ያልበዛበት በመሆኑ ምቹ ነበር የሚለው አትሌት ጉዲሣ ፣ በሌሎች የዓለም ክፍሎች ካደረግኳቸው የማራቶን ውድድሮች ጋር ሲነፃፀር ለየት የሚለው እና አስቸጋሪነቱ ከተማዋ ሞቃታማ በመሆኑ ብቻ ነው ብሏል፡፡ አሯሯጮች ቢኖሩ የተሻለ ሰዓት ማስመዝገብ ይቻል ነበር ያለው አትሌት ጉዲሣ ሸንተማ በቀጣይ እንዲስተካከል እጠብቃለሁ ብሏል፡፡ በኃይሌ ገ/ስላሴ ማራቶን ሳሸንፍ ያስመዘገብኩት ሰዓት በሌሎች የዓለም አገራት ከሚካሄዱ ትልልቅ ማራቶኖች በአንዱ ቢሆን 2 ሰዓት 06 በታች እንደገባሁ የሚቆጠር ነውም ብሏል፡፡
በአገሬ ህዝብ ፊት ባደረግኩት ውድድር ተደስቻለሁ አትሌት አልማዝ ነገደ
በሴቶች ምድብ የመጀመርያው የኃይሌ ገ/ስላሴ ማራቶን አሸናፊ ለመሆን የበቃችው አትሌት አልማዝ ነገደ ናት፡፡ ርቀቱን በ2 ሰዓት ከ39 ደቂቃ ከ50 ሰኮንዶች በሆነ ጊዜ ለመሸፈን ነው፡፡ በአገሬ ህዝብ ፊት ያደረግኩት ውድድር ነው ብላ ተደስታለች፡፡ አልማዝ ማራቶንን ለመጀመሪያ ጊዜ አምና የቡካሬስት ማራቶን በመሳተፍ ሲሆን አሸናፊ ነበረች፡፡ ዘንድሮ ደግሞ በአሜሪካ በተካሄዱ የግማሽ ማራቶን እና የጐዳና ላይ ሩጫ ውድድሮች ምርጥ ሰዓቶችን በማስመዝገብ ተሳክቶላታል፡፡
የኃይሌ ገ/ስላሴ ማራቶን አሸናፊነት ትልቅ መነቃቃት እንደፈጠረላት የተናገረችው አልማዝ፤ መሮጫው ጎዳና ሜዳማ እና አስፋልት መሆኑ ውድድሩን ደስ የሚል ውድድር አድርጐታል ብላለች ጥሩ ሰዓት ያላቸው አትሌቶች በብዛት አለመሳተፋቸውና አሯሯጭ አለመኖሩ የተሻለ ሰዓት ለማስመዝገብ ለነበራት ፍላጎት ተፅእኖ የፈጠረ ነበር፡፡ ማራቶኑ በአገር ውስጥ መዘጋጀቱ ውድድር ለሚፈልጉ አትሌቶች ጥሩ እድል መሆኑን የገለፀችው አትሌት አልማዝ ነገደ፤ ተመሳሳይ የማራቶን ውድድሮች በአገሪቱ የተለያዩ ከተሞች በብዛት መካሄዳቸው ለተተኪ አትሌቶች ሰፊ የውድድር እድል ስለሚጠቅሙ ያስፈልጋሉ ብላለች፡፡ በሃዋሣው የኃይሌ ገ/ስላሴ ማራቶን ተሳትፌ ያገኘሁት ውጤት በዓለም አቀፍ ውድድሮች ለመሳተፍ ይጠቅመኛልም ብላለች፡፡
ታላቁ ሩጫ በኢትዮጵያን ወደ ሌላ የእድገት ምዕራፍ አሸጋግሯል ሪቻርድ ኔሩካር
ታዋቂው እንግሊዛዊ አትሌት እና የአትሌቲክስ ባለሙያ ሪቻርድ ኔሩካር የኃይሌ ገ/ስላሴ ማራቶን ታላቁ ሩጫ በኢትዮጵያን ወደ ሌላ የእድገት ምዕራፍ አሸጋግሯል ይላል፡፡ ከዓመታት በፊት በታላቁ ሩጫ ኢትዮጵያ ስራ አስኪያጅነት የሠራ ነው እና አሁን ተቀማጭነቱን በእንግሊዝ አድርጎ ከተቋሙ ጋር መስራቱን የቀጠለው በኃይሌ ገ/ስላሴ ማራቶን ስኬታማነት ታላቁ ሩጫ ኢትዮጵያ በልምዱ ያበረከተው አስተዋጽኦ ከፍተኛ ሚና ነበረው፡፡ በማራቶን ውድድሩ 82 ተወዳዳሪዎች ከ16 የተለያዩ አገራት ለመምጣታቸው የአሜሪካው ሞራይ ማውንቴን ስፖርትስ ያደረገው እንቅስቃሴ ወሳኝ እንደነበር ሪቻርድ ኔሩካር፤ ተናግሯል፡፡ በማራቶን ውድድር በመሳተፍ የሚዝናኑ ስፖርተኞችን ከውጭ አገራት በማሰባሰብ የመጀመርያው ኃይሌ ገ/ስላሴ ማራቶን ስኬታማ ነበር ያለው ሪቻርድ፣ የውድድሩ ድባብ ጥሩ እንደነበር፣ የትራፊክ ፖሊስ፣ የፖሊስ አባላትና የከተማው ህዝብ ለውድድሩ የተቃና ሂደት የሰጡት ትብብር የሚመሰገን ብሏል፡፡ ውድድሩን በቀጣይነት ለማዘጋጀት ከፍተኛ ልምድ ተገኝቷል፡፡ የኃይሌ ገ/ስላሴ ማራቶን በማዘጋጀት ቱሪዝምንና ስፖርትን በማስተሳሰር ውጤታማ ለመሆን እንደሚቻል ተረጋግጧል፡፡ ኢትዮጵያ ውስጥ ባለ ድርጅት ትልቁን የማራቶን ውድድር በማዘጋጀት የሚከብድ ነበር ታላቁ ሩጫ በኢትዮጵያ የጎዳና ላይ ውድድሮችን በማዘጋጀት ያለውን የ13 ዓመታት ልምድ በመጠቀም ሰርቶ አቅሙን በመፈተሹ ወደፊትም በመላው ዓለም ከሚገኙ በአትሌቲክስ ውድድር አዘጋጅነት ከሚሰሩ ተቋማት እና ድርጅቶች ጋር በመተባበር ውድድሩን በየዓመቱ ለማካሄድ የሚያስችል አጀማመር ነው በማለት ለስፖርት አድማስ አስተያየት ሰጥቷል፡፡ ሃዋሣ የማራቶን ውድድር ለማዘጋጀት ከኢትዮጵያ ምናልባትም ብቸኛዋ ምቹ እና ተመራጭጥ ከተማ ናት ያለው ሪቻርድ ኔሩካር ወደፊት ምናልባትም ከ5 ዓመታት በኋላ በአዲስ አበባ ሌላ የማራቶን ውድድር ለማዘጋጀት ይሞከራል ብሏል፡፡

“ሁሉም አይስላንዳዊ መጽሐፍ ይወልዳል”
የሴቶች የፖለቲካ ፓርቲ ያላት ብቸኛ አገር ናት
በዲሞክራሲያዊ ተቋማት ጥንካሬ ከዓለም ሁለተኛ
በአንድ ፓርቲ ተመርታ አታውቅም - በጥምር ፓርቲዎች እንጂ

ባለፈው ሳምንት በዚሁ ጋዜጣ ላይ “አይስላንድ የደራሲያን ሀገር” በሚል ርዕስ ባቀረብኩት ጽሁፍ፣ ዋናውን ርዕሰ ጉዳይ ከማስረዳቴ በፊት ሀገሪቱን በሚገባ ለማወቅም ሆነ ለጠቅላላ እውቀት ይረዳሉ ያልኳቸውን የተለያዩ ጉዳዮች አቅርቤአለሁ፡፡ ይህ የዛሬው ጽሁፍ ካለፈው ሳምንት የቀጠለና የማጠቃለያ ጽሁፍ ነው፡፡
አይስላንድን በተመለከተ አለም አቀፉ ሚዲያ ሊያወራው የሚችለው ክፉም ሆነ በጐ ዜና እምብዛም አግኝቶ አያውቅም፡፡ ለአለም አቀፉ ሚዲያም ሆነ ለአብዛኛው የአለም ህዝብ አይስላንድ በቅዝቅዜና በበረዶ ግግር መካከል የምታንቀላፋ አንዲት ለሰሜን ዋልታ የቀረበች አውሮፓዊት ሀገር ማለት ናት፡፡ ከተጫናት ቅዝቃዜ መካከል አውጥቶና ላዩዋ ላይ የተጋገረውን በረዶ አራግፎ፣ በጥሞና ላያት ግን አይስላንድ የበርካታ አስገራሚ ታሪኮች ባለቤት የሆነች ሀገር ናት፡፡
የፖለቲካ ሳይንስ አጥኚዎች፤ “የአለማችን የፖለቲካ መድረክ እስከዛሬም ድረስ እጅግ በአብዛኛው ወንዶች በመሪ ተዋናይነት የሚተውኑበት መድረክ ነው” ይላሉ፡፡ አይስላንዳውያንን ግን በዚህ ሀሳብ ጨርሶ አይስማሙም፡፡
እንደ እውነቱ ከሆነ አይስላንዳውያን ባይስማሙ አይፈረድባቸውም፡፡ ለምን ቢባል? በአለማችን ውስጥ በሴቶች የተመሠረቱና በሴቶች የሚመሩ የፖለቲካ ፓርቲዎች ያሉዋት ብቸኛዋ ሀገር አይስላንድ ብቻ ናት፡፡ ዛሬ በምድረ አይስላንድ በማንኛውም አይነትና ሁኔታ የሚመሠረቱ ፓርቲዎች፣ አርባ በመቶ የሚሆነውን ኮታቸውን ለሴቶች የመመደብ ግዴታ አለባቸው፡፡ እ.ኤ.አ በ1980 ዓ.ም አይስላንዳውያን ባካሄዱት ብሔራዊ ምርጫ፣ ወይዘሮ ቪግዲስ ፊንቦጋዶቲርን ፕሬዚዳንታቸው አድርገው መርጠዋቸዋል፡፡ በዚህም በአለም በቀጥተኛ ህዝባዊ ምርጫ ለመጀመሪያ ጊዜ ሴት ፕሬዚዳንት የመረጡ ዜጐችና ሀገር ተብለው በአለም የፖለቲካ ታሪክ ውስጥ ለመመዝገብ በቅተዋል፡፡
እ.ኤ.አ በ2009 ዓ.ም ዮሀና ሲጐሮአርዶቲር፤ የአይስላንድ ጠቅላይ ሚኒስትርነቱን ስልጣን ጨበጡ፡፡ በዚህም አይስላንዳውያን ተጨማሪ የፖለቲካ ታሪክ ለመስራት በቁ፡፡ አይስላንድ ግብረ-ሠዶማዊነቷን በግልጽ ያወጀችን ፖለቲከኛ ጠቅላይ ሚኒስትር አድርጋ የሾመች በአለም የመጀመሪያዋ ሀገር ሆነች፡፡ በ2011 ዓ.ም የወጣ አለም አቀፍ ጥናት፤ በዲሞክራሲ ተቋማት ጥንካሬ አይስላንድን ከመላው አለም በሁለተኛ ደረጃ ሲያስቀምጣት፤ በመንግስቷ ግልጽነት ደግሞ ከአለም ሀገራት በአስራ ሶስተኛ ደረጃ ላይ መገኘቷን መስክሮላታል፡፡
ምርጫን በተመለከተ ጨርሶ ቀልድ የማያውቁ ዜጐች በድፍን አለም ውስጥ አሉ ከተባሉ አይስላንዳውያን ብቻ ናቸው፡፡ ብሔራዊ ምርጫ ሲደረግ የአይስላንዳውያን ዝቅተኛው ተሳትፎ በአማካይ 81.4 በመቶ ነው፡፡ በድፍን አለሙ እግር እስኪቀጥን ድረስ ሲያስሱ ቢኖሩ፤ እንደ አይስላንድ የፖለቲካ ፓርቲዎች ያሉ ከፍተኛ የህዝብ አመኔታ ያላቸው ፓርቲዎች ማግኘት ጨርሶ አይቻልም፡፡
አይስላንድ በሪፐብሊክነት ከተመሠረተችበት ጊዜ አንስቶ በተካሄዱት ህዝባዊ ምርጫዎች አንድም የፖለቲካ ፓርቲ አብላጫ ድምጽ አግኝቶ ብቻውን መንግስት ለመመስረት አለመቻሉ ከአይስላንድ አስገራሚ የፖለቲካ ታሪኮች አንደኛው ነው፡፡ እስከዛሬም ድረስ አይስላንድ የምትገዛው ወይም የምትተዳደረው በተለያዩ ፓርቲዎች በሚቋቋሙ የጥምር መንግስት ነው፡፡
የአለምን የመከላከያ ሠራዊት ሁኔታ የሚከታተሉ ባለሙያዎች፤ ስለ አይስላንድ የመከላከያ ሰራዊት ሁኔታ የሚያወሩት በመገረም ነው፡፡ አይስላንድ ኔቶ እየተባለ በአጭር ስሙ የሚታወቀው የሰሜን አትላንቲክ የጦር ቃል ኪዳን ድርጅት አባል ሀገር ናት፡፡ ይህ ጉዳይ በየትኛውም መመዘኛ ቢሆን ምንም የሚያስገርም ነገር የለውም፡፡ አስገራሚው ጉዳይ አይስላንድ የኔቶ አባል ሀገር የሆነችው አንድ መቶ እንኳ የማይሞሉ ቀላል የነፍስ ወከፍ መሳሪያ የታጠቁ ጠረፍ ጠባቂዎች በስተቀር አንድም የመከላከያ ጦር ሰራዊት ሳይኖራት መሆኑ ነው፡፡
ይህን ወታደራዊ ሁኔታ በማጤን የአይስላንድ የአየር ክልል “ማርያም ትጠብቀው!” ተብሎ የተተወ ነው ብላችሁ ልትገምቱ ትችላላችሁ፡፡ እውነታው ግን እንደዚህ አይደለም፡፡ የኔቶ አባል ሀገራት የጦር ሀይል የወራ ተራ እየገቡ የአይስላንድን የአየር ክልል ይጠብቃሉ፡፡ በአሁኑ ወቅት የአይስላንድን የአየር ክልል የሚጠብቀው የጣሊያን የአየር ሀይል ነው፡፡
የአለም አቀፍ ፖለቲካ ነገር ሲነሳ አይስላንዳውያን በ1986 ዓ.ም በዋና ከተማቸው ሬይካቪክ ታላቅ ጉባኤ በማዘጋጀት የአሜሪካው ፕሬዚዳንት ሮናልድ ሬገንና የሶቪየት ህብረቱ መሪ ሚካይል ጐርቫቾቭ የኒውክሊየር ጦር መሳሪያ ስምምነት እንዲፈራረሙ በማድረግ፣ ለአለም ሰላም የበኩላቸውን ከፍ ያለ አስተዋጽኦ ማድረጋቸውን በኩራት ይናገራሉ፡፡
የአለም ሰላምን በተመለከተ በየጊዜው የሚወጡ መረጃዎች፤ አይስላንድ ከአለም ሀገራት መካከል እጅግ ዝቅተኛ ወንጀል የሚፈፀምባት፣ እጅግ ከፍተኛ የፖለቲካና ማህበራዊ መረጋጋት ያለባት ሰላማዊ ሀገር እንደሆነች ይጠቁማሉ፡፡
ኢኮኖሚዋን በተመለከተ ያላት ታሪክም ጉደኛ ነው፡፡ ከሁለተኛው የአለም ጦርነት በፊት አይስላንድ ከአውሮፓ እጅግ ደሀ ሀገራት አንዷ ነበረች፡፡ አሁን ይሄ እንደ ተረት ወይም እንደ ጥንት ታሪክ የሚነገር ጉዳይ ነው፡፡ ዛሬ በአለም እጅግ ፍሬያማና ከፍተኛ የነፍስ ወከፍ አመታዊ ገቢ አላቸው ከሚባሉት ሀገራት አንዷ አይስላንድ ናት፡፡ የአለም አቀፍ የገንዘብ ድርጅት ከሁለት አመት በፊት ባወጣው ሪፖርት፤ የአይስላንድ አመታዊ የነፍስ ወከፍ ገቢ 54ሺ858 ዶላር መሆኑን አስታውቆ ነበር፡፡
እንግዲህ ልብ በሉ፡፡ እስካሁን የቃኘነው አይስላንድ በፖለቲካ፣ በኢኮኖሚ፣ በወታደራዊና፣ በአለም አቀፍ ግንኙነት ካሏት አሪፍ አሪፍ ታሪኮች በመጠኑ የተጨለፈ ነው፡፡ ከአገሪቱ ታሪኮች ከሁሉም የሚልቀውና አለምን ምንጊዜም አጀብ የሚያሰኘው ታሪኳ ግን በስነ ጽሁፍ ረገድ ያላት ታሪክ ነው፡፡ ይሄን ታሪኳን በአንድ አረፍተ ነገር መግለጽ ካስፈለገ “አይስላንድ ድንቅ የስነ ጽሁፍና የደራሲያን ሀገር!”
በየትኛውም አይነት አጋጣሚም ሆነ ምክንያት ወደ አይስላንድ እግሩ የጣለውና በጣት ከሚቆጠሩ አይስላንዳውያን ጋር “እንዴት ነህ? እንዴት ነሽ?” መባባል የቻለ ማንኛውም ሰው፤ በምንም ተአምር ቢሆን ሊያጋጥመው የማይችለው ሰው ቢኖር ደራሲ አይስላንዳዊ ብቻ ነው፡፡ ይህ ከቶ እንዴት ይሆናል፣ ብትሉ ነገሩ ቀላል ነው፡፡ ከአስር አይስላንዳውያን ውስጥ ቢያንስ አንዱ ወይም አንዷ መጽሐፍ ጽፎ ወይም ጽፋ ያሳተመ ወይም ያሳተመች ስለሆነ ነው፡፡
በዋና ከተማዋ ሬዳካቪክም ሆነ በሌሎች የአይስላንድ ከተሞች ዞር ዞር ብትሉ ቆጥራችሁ የማትዘልቁት የመጽሀፍት መሸጫ ሱቆችና አሳታሚ ኩባንያዎችን ታገኛላችሁ፡፡ በእነዚህ የመጽሀፍት መሸጫ ሱቆችና አሳታሚ ኩባንያዎች ግድግዳ ላይ ለአፍታ ያህል አይናችሁን ጣል ካደረጋችሁ ደግሞ በአይስላንዲክ ቋንቋ “አድ ጋንጋ ሜድ ቡክ አይ ማጋነም!” የሚል ጥቅስ በብዛት ተጽፎ ታገኛላችሁ፡፡ ትርጉሙ “ሁሉም አይስላንዳዊ መጽሀፍ ይወልዳል፡፡” ወይም በሁሉም አይስላንዳዊ ሆድ ውስጥ መጽሀፍ አለ፡፡” ማለት ነው፡፡
እንደ እውነቱ ከሆነ ይህን የአይስላንዳውያን ጥቅስ ማንም አሌ ብሎ ሊሞግተው የማይችለው ሀቅ ነው፡፡ ከጠቅላላው የአይስላንድ ዜጐች ውስጥ አስር በመቶ የሚሆኑት በዘመናቸው ቢያንስ አንድ መጽሀፍ ጽፈው ያሳተሙ ናቸው፡፡ በነፍስ ወከፍ ሲሠላ ከአይስላንዳውያን በስተቀር በርካታ መጽሀፎችን መፃፍና ማሳተም የቻሉ የሌላ ሀገር ዜጐችን ለሞት መድሀኒት ብላችሁ እንኳ በድፍን አለሙ ዞራችሁ ብትፈልጉ እስከወዲያኛው አታገኙም፡፡ መጽሀፎችን ገዝቶ በማንበብ ረገድም አይስላንዳውያን በመላው አለም አቻ የላቸውም፡፡ የስነ ጽሁፍ ህትመቶችን ወደ ሀገራቸው በማስመጣትም አይስላንዳውያን የአለም ቁንጮ ናቸው፡፡
አይስላንዳውያን ደራሲያን ብቻ አይደሉም። የሌሎች ሀገራት ደራሲያንን የስነጽሁፍ ስራዎች በመተርጐም በኩልም የሚስተካከላቸው አንድ ሀገር እንኳ አለማችን ማግኘት አልቻለችም። በነፍስ ወከፍ ሲሰላ እጅግ ከፍተኛ የመጽሀፍ መሸጫ መደብር በመያዝ አይስላንድን በልጦ የአለም ቁንጮ መሆን የቻለ አንድም ሌላ ሀገር እስከዛሬ ድረስ ሊገኝ አልቻለም፡፡
በሬይካቪክ ከተሞች ባሉ የህዝብ መናፈሻ ቦታዎች ውስጥ ያሉ ሁሉም መቀመጫዎች ስማርት ፎን ያላቸው ሰዎች የተለያዩ የመጽሀፍት ትረካዎችን ማዳመጥ እንዲችሉ ተደርገው በእውቅ የተሰሩ ናቸው፡፡ በዚህ የተነሳም ዩኔስኮ ከተማዋን ሬይካቪክን “የስነጽሁፍ ከተማ” ብሎ ለመሰየም በእጩነት መዝግቦ ይዟታል፡፡
በአይስላንድ እንግዳ የሆነና ፀጉሩን ለመቆረጥ ወደ ፀጉር ቤት ጐራ ያለ ማንኛውም ሰው በመጀመሪያም ሆነ በመጨረሻ የሚቀረብለት ጥያቄ፣ እንደኛ ሀገር ፀጉር ቤቶች የአርሴናል ወይም የማንቸስተር ጉዳይ ሳይሆን ስለ አነበባቸው መጽሀፍቶችና በሀገሩ ስለታተሙ አዳዲስ መጽሀፍቶች ብቻ ነው፡፡
አይስላንድ በአለም ደረጃ የታወቁ ደራሲያንን ማፍራት ችላለች፡፡ ከእነዚህ እውቅ አይስላንዳዊ ደራሲዎች ውስጥ በ1955 ዓ.ም በስነጽሁፍ የኖቤል ሽልማት ያገኘው ደራሲ ሀልዶር ላክስነስ ይገኝበታል፡፡ ሲቲን ስቲይናር የተባለው አይስላንዳዊ ደግሞ የሀያኛው ክፍለ ዘመንን መቆጣጠር የቻለ የዘመናዊ ቅኔ ባላባት ነበር፡፡
በመጨረሻ ጉዳያችንን ለማጠቃለል አንድ ጥያቄ እናቅርብ:- “አይስላንድ ከሌሎች ሀገራት በተለየ ዘመን የጠገበ የስነጽሁፍ ታሪክ ባለቤትና የአለማችን ቁንጮ የስነጽሁፍና የደራሲያን ሀገር ልትሆን የቻለችበት ምክንያት ለመሆኑ ምንድን ነው?” ወጣቱ አይስላንዳዊ ቢዬን ሲጉርድሰን ስለዚህ ጉዳይ ሲገልጽ፤ “ሀገራችን አይስላንድ የታሪክ ተራኪዎች ሀገር ናት፡፡ ሲመሽና ቅዝቃዜው ሲበረታ ሰብሰብ ብለን ታሪክ ከመተረክና ሲተረክ ከማዳመጥ በቀር ሌላ ስራ እኮ የለንም!” ለጊዜው ከዚህ የተሻለ መልስ የምናገኝ አይመስለኝም፡፡

በኢቴቪ የምናያቸው ቪዲዮዎችና ምስሎች፣ የተደፈጠጡና የተጣመሙ ሆነዋል - ስንት ወሩ? አልተስተካከለም።
በኢቴቪ የሚሰራጩ የተዛቡና የተሳሳቱ ዜናዎች ወይም ዘገባዎች ያሳፍራሉ፤ ደግሞም መላ ያለው አይመስልም።

አንዳንዴ፣ በኢትዮጵያ ሬድዮና ቴሌቪዥን የሚሰራጩ ዜናዎችን መስማት ያሳቅቃል፤ ወይም ያዝናናል። በሌላ በኩል ደግሞ ቀሽም ስህተት ስለሆነ ያዝናናል። ከግማሽ ምዕተ አመት በላይ እድሜ ያስቆጠሩ የአገሪቱ ብቸኛ የቴሌቪዥንና የሬድዮ አንጋፋ ድርጅቶች መረጃ ሲሳሳቱና ሲያዛቡ ማየት ያሳቅቃል።
ባለፈው ረቡዕ ምሽት የተሰራጨውን ዜና መጥቀስ እችላለሁ። በአፍጋኒስታን የተሰማራው ሰላም አስከባሪ ሃይል አገሪቱን ለቅቆ የሚወጣበትን የጊዜ ገደብ ለመቁረጥ እንዳልቻለ የሚገልፅ ነው ዜናው። ሰላም አስከባሪው ሃይል ወደ አፍጋኒስታን የተሰማራው፣ በእርስበርስ ግጭት መነሻነት እንደሆነም ዜናው ይጠቅሳል። የአሜሪካ እና የአጋሮቿ ጦር ሃይል ወደ አፍጋኒስታን ለምን እንደተሰማራ ተረሳ ማለት ነው? አስር አመት ያስቆጠረ ዘመቻ ስለሆነ ኢቲቪ አያስታውሰው ይሆናል፡፡ ግን፤ እንዴት እንዴት የቢን ላደንና የአልቃይዳ ሽብር ሊረሳ ይችላል? በኒውዮርክና በዋሺንግተን የ3ሺ ሰዎችን ህይወት የቀጠፈ የሽብር ጥቃት መፈፀማቸውስ እንዴት ይዘነጋል? ከዚያ በኋላ፣ በአሜሪካ መሪነት፣ በመቶ ሺ የሚቆጠሩ ወታደሮች ወደ አፍጋኒስታን መዝመታቸውን መላው አለም ያውቀዋል፡፡

ለኢቲቪ እንዴት እንደተሰወረበት እንጃ! አናስታውስም? ለአመታት በመንዛዛቱ “ዘመቻነቱ”ና ውጤታማነቱ ቢደበዝዝም፣ በጊዜው ትክክለኛ እርምጃ ነበር።
የሆነ ሆኖ፣ የአሜሪካ ዘመቻ ቢን ላደንን ለመግደል፣ አልቃይዳን ለመውጋትና ጥላ ከለላ የሆናቸውን የታሊባንን ሃይል ከስልጣን ለማስወገድ እንጂ፣ “ሰላም ለማስከበር” የተካሄደ ዘመቻ አይደለም። በአጭሩ፣ ለጦርነት ነው፣ አሜሪካና አጋሮቿ ወታደሮቻቸውን ያዘመቱት። በእርግጥ ከጊዜ ወደ ጊዜ የወታደሮቹ ቁጥር ቀንሷል። ነገር ግን፣ ዛሬ ከአስር አመት በኋላም፣ ገሚሶቹ ከአሜሪካ፣ ቀሪዎቹ ደግሞ ከሌሎች የኔቶ አባል አገራት የተውጣጡ ወደ መቶ ሺ የሚጠጉ ወታደሮች በአፍጋኒስታን እንደተሰማሩ ናቸው። ሰላም አስከባሪ የሚሰማራው ደግሞ፣ “ሰላም ሰፍኗል” ተብሎ ሲታሰብ ነው - “ሰላምን ለመጠበቅ”። የተባበሩት መንግስታት ሰላም አስከባሪ ሃይል ወደ ሶማሊያ ያልተሰማራው ለምን ሆነና? በአገሪቱ ሰላም የለም፣ ሰላም ከሌላ ሰላምን ማስከበር አይቻልም በሚል ነው። ታዲያ የአፍሪካ ህብረት፣ ለምን “ሰላም አስከባሪ ሃይል” አሰማራ? “የተወሰነ ሰላም ተገኝቷል” ብሎ ስላመነ ነዋ።
በአፍጋኒስታን ግን፣ የሰላም አስከባሪ ሃይል የማሰማራት ሃሳብ በጭራሽ ተነስቶ አያውቅም። ሰሞኑን ስለ አፍጋኒስታን እና ስለ አሜሪካ ወታደሮች የሚያወሱ በሺ የሚቆጠሩ ዜናዎችና ዘገባዎች ቢሰራጩም፣ በአንዳቸውም ላይ “ሰላም አስከባሪ ሃይል” የሚል አባባል አታገኙም - በኢትዮጵያ ሬድዮና ቴሌቪዥን ድርጅት በተሰራጨው ቀሽም ዜና ካልሆነ በቀር። በእርግጥ፣ ዜናውን የሰራው ጋዜጠኛ ቀሽም ላይሆን ይችላል። ደግሞም፣ በዜናው የተካተቱ በርካታ መረጃዎች ሲታዩ፣ ጋዜጠኛው ቀሽም እንዳልሆነ ይጠቁማሉ። ቀሽም ስህተት እንዳይፈጠር የሚከላከል አሰራርና ባህል በድርጅቱ ውስጥ አለመኖሩ ይመስለኛል - ዋናው ችግር።
“የሜርከል ፓርቲ አሸነፈ፣ ፓርቲያቸው ተሸነፈ”
በቅርቡ በጀርመን በተካሄደው ምርጫ በአብላጫ ድምፅ ያሸነፈውና በአንጌላ ሜርከል የሚመራው ፓርቲ፤ አዲስ መንግስት ለመመስረት ውይይት እያካሄደ ነው። ሲዲዩ የተሰኘው ፓርቲ ከነአጋሩ፣ በምርጫው 42 በመቶ ድምፅ አግኝቷል። ታዲያ በኢትዮጵያ ቴሌቪዥንና ሬዲዮ የተሰራጨው ዜና ምን ይላል አትሉም? ቀደም ብሎ እንደተጠበቀው የአንጌላ ሜርከል ፓርቲ በምርጫው ሲያሸነፍ፣ ተፎካካሪው ሲዲዩ ፓርቲ 42 በመቶ ድምፅ በማግኘት ተሸንፏል ይላል ዜናው። ትክክል ይመስላል። ከሃምሳ በመቶ በታች ድምፅ ያገኘ ፓርቲ በተሸናፊነት መጠቀሱ አይገርምም። ቀሽሙ ስህተት ምን መሰላችሁ? ሲዲዩ የአንጌላ ሜርከል ተፎካካሪ ፓርቲ አይደለም፤ አንጌላ ሜርከል የሚመሩት ፓርቲ ነው። አሸነፈ እንጂ አልተሸነፈም፡፡ በኢቴቪ አዘጋገብ…”አቶ ኃይለማርያም የሚመሩት ፓርቲ በምርጫው ሲያሸንፍ ኢህአዴግ ተሸንፏል” እንደማለት እኮ ነው፡፡
የአንጌላ ሜርከል ፓርቲ (ሲዲዩ) ከነአጋሩ 42 በመቶ ድምፅ በማግኘቱ ነው፣ በአብላጫ ድምፅ አሸናፊ ለመሆን የቻለው። ዋናው ተፎካካሪ ፓርቲ (ኤስፒዲ) ደግሞ 25 በመቶ ገደማ ድምፅ አግኝቷል። 9 በመቶ፣ 8 በመቶ፣ እና ወደዚያው ገደማ ድምፅ ያገኙ ሌሎች ፓርቲዎችም አሉ። የአንጌላ ሜርከል ፓርቲ በአሸናፊነት የሚጠቀሰው፣ መንግስት ለመመስረት ከአንድ ፓርቲ ጋር ጥምረት መፍጠር ስለሚበቃው ነው። ተቀናቃኛቸው ኤስፒዲ ፓርቲ ግን፣ ከአራት ወይም ከአምስት ፓርቲዎች ጋር ጥምረት ካልፈጠረ፣ መንግስት ለመመስረት የሚያስችል አቅም አይኖረውም። እንግዲህ፣ የአንጌላ ሜርከል ፓርቲ በአብላጫ ድምፅ ሲያሸንፍ፣ ተፎካካሪው ሲዲዩ ፓርቲ 42 በመቶ ድምፅ ተሸንፏል የሚለው ዜና፤ በቀሽም ስህተት ሳቢያ ምን ያህል መረጃውን ሁሉ እንዳዛባው አያችሁ?
የአካባቢው ጥበቃ ሟርትና የዩኤን እዬዬ
በዚሁ ወር የተሰራጨ ሌላ ዜናም ልጥቀስላችሁ። “ከአካባቢ ጥበቃ” ጋር. በተያያዘና የአለም የሙቀት መጠንን በተመለከተ በተባበሩት መንግስታት ድርጅት ስር፣ በየጊዜው ጠቅላላ “ሳይንሳዊ” ሪፖርት አዘጋጅቶ የሚያቀርብ ድርጅት አለ። በእርግጥ፣ የአካባቢ ጥበቃ ጉዳይ፣ በአመዛኙ “ከፖለቲካ እምነት” ጋር እንጂ፣ “ከሳይንሳዊ እውነታ” ጋር ብዙም አይዛመድም። ምን ለማለት እንደፈለግኩ ልንገራችሁ፡፡ “ሟርት” ማስተጋባት የማይሰለቻቸው የአካባቢ ጥበቃ ቡድኖች፤ ከሰላሳ አመት በፊት፣ “አለም በቅዝቃዜ ደንዝዛ በበረዶ ትሸፈናለች” በማለት ነበር ዘመቻ የሚያካሂዱት። ነገር ግን፣ የተነበዩለት “Global Cooling” በእውን አልተከሰተም። ግን ሌላ ትንበያ አላጡም። አለምን የሚያሰጋት፣ የበረዶ ቅዝቃዜ ሳይሆን፣ የዓለም ግለት “Global Warming” ነው ተባለ።

በእርግጥም፣ የአለም አማካይ ሙቀት፣ በመቶ አመታት ውስጥ በግማሽ ሴንቲግሬድ እንደጨመረ የተለያዩ የሳይንስ ምርምሮች ይመሰክራሉ። የአካባቢ ጥበቃ ቡድኖች ግን፣ ሳይንሳዊ ግኝት ላይ ሳይሆን፣ ከሟርት ያልተለየ ትንበያ ላይ ነው የሚያተኩሩት። በመቶ አመታት ውስጥ የአለም ሙቀት እስከ 5 ዲግሪ ሴንቲግሬድ ይጨምራል በማለት አለምን የሚያስበረግግ “እዬዬ” ማስተጋባት፣ የቡድኖቹ የእለት ተእለት ስራ ነው። “እዬዬ”ውን በአስለቃሽነት እያስተባበረ የሚመራው ደግሞ የተባበሩት መንግስታት ድርጅት ነው - በየጊዜው በሚያዘጋጃቸው ጠቅላላ “ሳይንሳዊ” ሪፖርቶች።
የ“ሟርት” ነገር! ዩኤን እና የአካባቢ ጥበቃ ቡድኖች የተነበዩት ያህል የአለም ሙቀት አልጨመረም። በተለይ ባለፉት 20 አመታት፣ ከቁጥር የሚገባ ጭማሪ አላሳየም። ለዚህም ይመስላል፣ “የአለም ግለት” ከሚለው ስያሜ ይልቅ፣ በደፈናው “የአየር ንብረት ለውጥ” “Climate Change” የሚል ፈሊጥ ያመጡት። አምስተኛው ጠቅላላ “ሳይንሳዊ” ሪፖርት በቅርቡ የተሰራጨውም፣ በዚህ ድፍን ስያሜ ነው። ከቀድሞዎቹ ሪፖርቶች ብዙም የተለየ አይደለም፤ ትንሽ ለየት የሚለው፣ ባለፉት 20 አመታት የአለም ሙቀት እንደተጠበቀው አለመጨመሩን ለመካድ አለመድፈሩ ብቻ ነው። ከተጠበቀውና ከተተነበየው ጋር ሲነፃፀር፣ ከሶስት እጥፍ በታች ነው የሙቀት ለውጥ የተመዘገበው። ከሪፖርቱ ጋር በተያያዘ የተሰራጩ ዓለማቀፍ ዘገባዎችም፣ ይህንን አወዛጋቢ መረጃ በስፋት ጠቅሰውታል። የኢትዮጵያ ሬዲዮና ቴሌቪዥን ድርጅት (ኢሬቴድ) ግን፣ ጨርሶ ጉዳዩን አላነሳም። እናስ ምን ዘገበ? በተባበሩት መንግስታት አስተባባሪነት የሚሰራጨው ሪፖርት ውስጥ የተካተቱ የዓለም ግለትን የሚመለከቱና ዓለምን የሚያስበረግጉ ወሬዎችን ነዋ። ግን ምን ዋጋ አለው? የኢትዮጵያ ሬዲዮና ቴሌቪዥን ድርጅት እነዚህን ጎደሎ መረጃዎችንም ቢሆን በትክክል አልዘገባቸውም። እንዴት በሉ።
እንደሚታወቀው፣ በዩኤን እና በአካባቢ ጥበቃ ቡድኖች ድምዳሜ መሰረት፣ የአለም ግለት መንስኤ የሰዎች አኗኗር ነው። በተለይም በነዳጅ አጠቃቀም የሚፈጠረው ካርቦንዳይኦክሳይድ፣ ለአለም ግለት ዋነኛ መንስኤ ነው ይላሉ።

ምን ያህል እርግጠኞች ናችሁ ተብለው ሲጠየቁ፣ በአብዛኛው እርግጠኛ ሆነናል የሚል ምላሽ ነበር የሚሰጡት። ከቅርብ አመታት ወዲህ ደግሞ፣ “በጣም እርግጠኞች ነን፤ 90 በመቶ እርግጠኞች ነን” ወደ ማለት ደረሱ። በዘንድሮው ሪፖርት ደግሞ፣ “እጅግ በጣም እርግጠኞች ነን” ወደ የሚል ደረጃ ተሸጋግረዋል። የአለም ግለት በሰዎች አኗኗር ሰበብ እንደተከሰተ 95 በመቶ እርግጠኞች ሆነናል ይላል ሪፖርቱ። የኢትዮጵያ ሬዲዮና ቴሌቪዥን ድርጅት ግን፤ የአለም ግለት 95 በመቶ ያህሉ በሰዎች አኗኗር ሰበብ የሚከሰት ነው ብሎ ዘገበው። ምን እንደማለት መሰላችሁ? “የእገሌ ቡድን የተሸነፈው በተጨዋቾች አሰላለፍ ሳቢያ እንደሆነ እርግጠኛ ነኝ፤ 95 በመቶ እርግጠኛ ነኝ” ሲባልና፣ “የእገሌ ቡድን ለሽንፈት የተዳረገበት ምክንያት 95 በመቶ ያህሉ ከተጫዋቾች አሰላለፍ የመነጨ ነው” ሲባል ልዩነት የለውም?
ምናልባት ይህንን ልዩነት ማወቅ ይከብድ ይሆናል። አንዳንዴ ግን፣ የኢቴቪ ቀሽም ስህተቶች የሚመነጩት ካለማወቅ ብቻ አይደለም። ይህችን ቅንጣት ስህተት ተመልከቱ። ጠ/ሚ ኃይለማሪያም ደሳለኝ፣ በኒውዮርክ ከተለያዩ ባለሃብቶች ጋር ባደረጉት ውይይት ስለኢትዮጵያ ኢኮኖሚና ስለኢንቨስትመንት እድሎች ገለፃ አድርገው አልነበር? በውይይቱ የተሳተፉ አንድ ባለሃብት፣ ለኢቴቪ አስተያየታቸውን ሲሰጡ፣ በገለፃው “intrigued” ሆኛለሁ አሉ - በእንግሊዝኛ። በኢቲቪ ሲተረጎም፣ “በገለፃው ተደስቻለሁ” ተብሎ ቀረበ። የባለሃብቱ አነጋገር ግን፣ “ገለፃው ትኩረቴን ስቧል”፤ “ገለፃው፣ የማወቅ ጉጉት አሳድሮብኛል” ከሚል ሃሳብ ጋር የጥርጣሬ ስሜትንም ጭምር የሚያስተላልፍ ነው። “ገለፃው ጥያቄ አጭሮብኛል” እንደማለት አይነት። ይሄ ነው፤ “በገለፃው ተደስቻለሁ” ተብሎ የተተረጎመው። የአላዋቂነት ስህተት ነው ወይስ ከፕሮፓጋንዳ ፍቅር የሚመነጭ ስህተት? የሆነ ሆኖ ስህተት ነው።
እንግዲህ፣ በጥቂት የዜና ስርጭቶች ውስጥ የታዘብኳቸው ቀሽም ስህተቶችን ነው ያካፈልኳቸው፡፡ ታዲያ እነዚህን ስህተቶች ማስተካከል ለኢቴቪ ይከብደዋል? ላይ ላዩን ስታዩት ከባድ አይመስልም። ነገር ግን፣ ወጣትና ጎበዝ ጋዜጠኞች የሚያጋጥሟቸው ቀሽም ስህተቶችን ማስተካከል የሚቻለው፣ ሙያውንና ሙያተኛውን የሚያበለፅግ አሰራር በማዳበር ነው። ይሄ ደግሞ ከባድ ነው። የረዥም ጊዜ ጥረትንና ፅናትን ይጠይቃል። ታዲያ ይሄ ነገር ኢቴቪ ውስጥ ይኖራል ተብሎ ይታሰባል? አይመስለኝም። የመንግስት ድርጅት ነዋ፡፡
ሌላውን ተዉት። ኢቴቪ የዜና እና የዘፈን ክሊፖችን ሳይቀር፣ ምስሎችንና ቪዲዮዎችን እየደፈጠጠ ማሰራጨት ካዘወተረ ስንት ወሩ ነው? የተለያዩ የቪዲዮ ፎርማቶች፣ በቁመታቸውና በወርዳቸው እንደሚለያዩ ማወቅኮ፣ የቴሌቪዥንና የቪዲዮ ‘ሀሁ’ ነው። በአንዱ ፎርማት የተዘጋጀ ቪዲዮ፣ በሌላ ፎርማት ከተሰራጨ… ወይ የተደፈጠጠ ድንክ ይሆናል ወይም ወደ ላይ የተመዘዘ ሞላላ ሆኖ ይታያል። ያው እንዳያችሁት የስንቱ ሰው መልክና ቁመና፣ በኢቴቪ ሲደፈጠጥ ከርሟል። አሁን፣ ቪዲዮዎችን በትክክለኛ ፎርማት ማሰራጨት ትልቅ ስራ ሆኖ ነው? ግን ለወራት አልተስተካከለም። ይህችን ለማስተካከል የሚበቃ የአፍታ ጥረትና ፅናት ካልተገኘ፤ ሌሎችን ስህተቶች ለማረም የረዥም ጊዜ ጥረትና ፅናት ከወዴት ይመጣል?

 

አንድ እሥር ቤት ውስጥ የሆነውን ነገር ቆይተው ሲያስቡት ተረት እንጂ በዕውነት በታሪክ የተከሰተ አይመስልም፡፡
የእሥር ቤቱ ክፍል አራት በአራት ነው ፡፡ ከሃምሣ እስከ ስልሣ የሚሆኑ እሥረኞች ታጭቀውበታል፡፡ የሚተኙት እንደጨፈቃ ተጨፍቀው ነው፡፡ ጠዋት ሲነጋ ቀኑን ለመግፋት ዳማ፣ ዶሚኖ፣ ቼዝ እና እዚያው በተሠራ ወረቀት ካርታ ይጫወታሉ፡፡
የእሥረኛው ዓይነት እንደየጉዳዩ የተለያየ ነው፡፡ በፖለቲካ የታሠረ አለ፡፡ በኢኮኖሚ (ገንዘብ ነክ) ጉዳይ የሚመጣ አለ - ደረቅ ወንጀል ይሉታል፡፡ በእግሩ ድንበር አልፎ ለመሄድ ሲሞክር ተይዞ የሚታሠር አለ “እግር እላፊ” ይሉታል በእሥረኞቹ አጠራር፡፡ የዘማች ሚስት በማማገጥ የሚታሠር አለ “ጭን እላፊ” ይሉታል፡፡ በስርቆሽ የሚታሠር አለ “እጅ - እላፊ” ይሉታል፡፡ በዘለፋ፣ መንግሥት (መሪ) በመሰደብ የሚታሠር አለ - “አፍ -እላፊ” ይሉታል፡፡
እሥር ቤቱ ክፍል አሁን ዳማ የማጫወቱት ሁለት ሰዎች፤ አዕምሮአቸውን ነካ የሚያደርጋቸው ናቸው፡፡ በአፍ - እላፊ ነው የታሠሩት፡፡ ዳማ እየተጫወቱ ይወያያሉ፡፡
“ይሄ መንግሥት ዕብድ ማሠሩ አይገርምህም?” ይላል አንደኛው፡፡
“አሣሪው ይሁን ታሣሪው ዕብዱ? ገና አልለየምኮ” ይላል ሁለተኛው፡፡
“እኔ መንግሥት ይመስለኛል ዕብድ”
“እኔ ግን እኛ ዕብድነታችንን ቢያዘልቅልን ከመንግሥት እንሻላለን እላለሁ”
“ይልቅ ዳማችንን እንጫወት፡፡ ለሁላችንም የሚሻለን፤ ህዝብ ቢያብድ ነበር”
“ለምን?”
“አለዛ ድንዝዝ ፍዝዝ ብሎ ይቀራላ!”
“በል እሺ ዳማችንን እንጫወት?”
ዳማቸውን መጫወታቸውን ይቀጥላሉ፡፡
አንደኛው የሌላኛውን ንጉሥ፤ በወታደርም፣ በንጉሥም የሚበላት ሁኔታ ይፈጠራል፡፡
ሁለተኛው - “በንጉሥ ትገደዳለህ፡፡ ንጉሤን በንጉሥ ነው እንጂ በወታደር አትበላኝም” ይላል፡፡
አንደኛው - “በየትኛውም ብበላህ ጨዋታው ያልቃል፡፡ በፈለኩት እበላለሁ”
ሁለተኛው - “በጭራሽ! በንጉሥ ትገደዳለህ”
አንደኛው - “እኔ እምልህ፤ አንዴ ሞት ከተፈረደብህ በቺቺ ግደሉኝ በክላሽ ግደሉኝ እያልክ ምን ያጨቃጭቅሃል?” አለው፡፡
* * *
በትንሹም በትልቁም ነገር ከማበድ ይሰውረን፡፡ የመሞቻ መሣሪያ ከማማረጥ ያድነን፡፡ የፖለቲካ፣ የኢኮኖሚና የማህበራዊ እንከኖቻችን ጥቅል ውጤት ማስጨነቁና ማሳሰቡ የሀገርና የህዝብ ስሜት ላለው ሁሉ አይቀሬ ነው፡፡ በተለይም ዱሮ የእጅ - እላፊ ይባል የነበረው የምዝበራና አገርን የማራቆት ተግባር፣ (ዛሬ ሙስና የተባለውን)፤ “ባንዱ ያለማ ባንዱ ያደለማ” ሆኗል፡፡ አገር ትልቅ ለውጥ ላይ ናት፤ ከፍተኛ የትራንስፎርሜሽን ሂደት ላይ ነን እየተባለ፤ በጐን የዝርፊያ የኮንትሮባንድ እና “በአንድ ጀንበር ፎቅ ሠርቼ ልደር” ዓይነት ዘመናዊ ምዝበራ ይታያል፡፡ “በአንዴ ዘጋ/ዘጋች” ዛሬ የተለመደ ቋንቋ ነው፡፡ እንደነናይጄሪያና እንደነናይሮቢ (“ናይሮበሪ” እንደተባለው) ዐይን - ያወጣ የቀን ተቀን ዘረፋ የሚመጣው ከላይ እስከታች እየተወሳሰበ ያለው ሙስና ፍፁም ወደፈጠጠ ደረጃ ሲደርስ ነው፡፡ “ልጄን የእንቁላሉ ዕለት ቆንጥጬው ቢሆን በሬ ሲሰርቅ አይያዝም ነበር” አለች እንደሚባለው ነው፡፡
አንድም ሙስናው በየአቅጣጫው መሆኑ፤ አንድም ደግሞ ቢሮክራሲያዊ መጠቅለያ መኖሩ እጅግ ውስብስብ ያደርገዋል፡፡ (ዱሮ “ቢሮክራሲያዊ ካፒታሊዝም ይውደም” የሚል መፈክር ነበር፤ ነብሱን ይማረው!) በዚህ ላይ የግለሰቦች አሻጥር ሲጨመርበት፣ ከቁጥጥር ውጪ ወደሆነ ደረጃ ይሸጋገራል፡፡ የመሬት አሰቃቂ አወሳሰድ፣ ከፍተኛ የኮሚሽንና የድለላ ሥራ፣ አደገኛ ወገናዊ አሠራር…በአስደንጋጭ የድህነት መቀመቅ ውስጥ ለገባች አገር ከምትሸከመው በላይ ትከሻ አጉብጥ ሸክም ይሆንባታል፡፡ የባሰ ዘግናኝ የሚሆነው ደግሞ ከዕለት ወደ ዕለት በምዝበራ ምክንያት መታሰር ራሱ እየተለመደና ቀላል እየመሰለ መምጣቱ ነው፡፡ “እገሌ ታሠረኮ” ሲባል፤
“ተወው በልቷል - የሚበቃውን ቀለብ አከማችቷል”
ማለት እንደሰላምታ የሚነገር መሆኑ አሳዛኝ ነው፡፡
ዱሮ “በሥራው አጋጣሚ በእጁ የገባውን የመንግሥት ገንዘብ ለግል ጥቅሙ በማዋሉ” የሚለው ሐረግ ነበር ሬዲዮንና ቴሌቪዥን ያጣበበው፡፡ ዛሬ ዳር እስከዳር በየሰው አፍ የሚወራ ነገር ሆኗል፡፡ ዝርፊያው ዓይነት በዓይነት ሆኗል፡፡ ተወርቶም በቀላሉ ይረሳል፡፡ በተለይ ለህብረተሰብ ቀጥተኛ መጥፊያ የሚሆኑ እንደመድሃኒት ያሉ የኮንትሮባንድ ዕቃዎች ባመቸው መንገድ ሁሉ ተበርዘው ከተባዙ፣ ምን ያህል አሰቃቂ የሆነ ዕልቂት እንደሚያስከትሉ መገመት አያዳግትም፡፡ የሚያስገኙት ገንዘብ የትየለሌ፣ የሚፈጁት ህዝብ የትየለሌ!!
ማናቸውንም የጥፋት ድርጊት የሚፈጽሙ ወገኖች ለሀገር እንደቆሙ፤ የህዝብ ልጆች እንደሆኑ አድርገው መጮሃቸውና ሀቀኛ መምሰላቸው፤ ሌላው እንዳይናገር በር ይዘጋል፡፡ They shout at most against the vices they themselves are guilty of እንደሚሉት ነው ፈረንጆቹ - ጅራፍ እራሱ ገርፎ እራሱ ይጮህ እንደማለት ነው፡፡ ጩኸቱ በቅጡ ለገባው አገር - ወዳድ ሰው ግን፤ “ቤቱን አቃጥሎ እንዴት ብሩህ ቀን እንደሆነ ተመልከቱ” አለ እንደተባለው ነው፡፡ ልዩነቱ ያኛው ለግሉ እየተጠቀመ፤ ይሄኛው የገዛ ንብረቱን ጭምር እያወደመ የሚጃጃል መሆኑ ነው፡፡ ሁለቱንም መዋጋት ተገቢ ነው!

ሜጀር ጀነራል አደም መሀመድ የአየር ሀይል አዛዥ ሆነው መሾማቸውንና የአዛዥ ጄነራሎች ላይም የምደባ ለውጥ መደረጉን ምንጮቻችን አመለከቱ፡፡ በአየር ሀይል አዛዥ በነበሩት ሜጀር ጀነራል ሞላ ሀይለማርያም ምትክ የተሾሙት ሜጀር ጀነራል አደም የአየር ሀይል ፓይለት የነበሩና በሱዳን አቢዬ ግዛት የሠላም አስከባሪ ሀይል ምክትል አዛዥነት ያገለገሉ እንዲሁም የመከላከያ ዘመቻ መምሪያ ኃላፊ ነበሩ፡፡
በሌሎች የመከላከያ የስራ ምድብ ቦታዎች ላይ የአዛዦች የምደባ ለውጥ መደረጉን የተናገሩት ምንጮች፣ አዲስ የሀላፊነት ምደባ ከተሠጣቸው ውስጥ ሌተናል ጀነራል ሠአረ መኮንን፣ ሌተናል ጀነራል አበባው፣ ሜጀር ጀነራል ዮሀንስ ወልደጊዮርጊስ፣ ሜጀር ጀነራል ገብራት አየለ እና ሌሎችም ይገኙበታል፡፡
ባለፈው አመት እና ዘንድሮ ከ60 በላይ ለሚሆኑ መኮንኖች የጀኔራልነት ሹመትና እድገት መሰጠቱ ይታወሳል፡፡