Administrator

Administrator

በኢትዮጵያ ደራስያን ማኅበርና በብርሐንና ሰላም ማተሚያ ድርጅት በጋራ አስተዳደር ተዟዟሪ ሂሳብ ለህትመት የበቃው ‹‹ፍቅርና ተስፋ›› የተሰኘው የተሾመ ወልደሥላሴ ረጅም ልቦለድ፣ ሰሞኑን ለገበያ ቀረበ፡፡ ልቦለዱ፣ ከ1960ዎቹ ጀምሮ የነበረውን የሀገሪቱን ማህበራዊ፣ ፖለቲካዊ፣ ባህላዊና ሥነልቦናዊ ጣጣዎችን በመተረክ፣ ለገነገኑ ሀገራዊ ችግሮች መፍትሔ የሚጠቁም አስተሳሰቦች የተንጸባረቁበት እንደሆነ ተጠቁሟል፡፡ መጽሐፉ፣ 380 ገጾች ያሉት ሲሆን፣ ዋጋው 55 ብር እንደሆነ ታውቋል፡፡
በኤርሚያስ መኮንን የተጻፈው፣ 178 ገጾች ያሉት ‹‹አጋምና ቁልቋል›› ረጅም ልቦለድም ባለፈው ሳምንት ለንባብ በቅቷል፡፡ መጽሐፉ በሽፋኑ ላይ፣ ‹‹በእውነተኛ ታሪክ ላይ የተመሰረተ ልብ-ወለድ›› ስለመሆኑና ‹‹ የትዳር ተጣማሪዎች በአሜሪካ የሚያጋጥማቸውን ችግርም ቁልጭ አድርጎ ያሳያል›› ሲል ጠቁሟል፡፡ በውሥጥ ገጹ ላይ ደግሞ፣ ባልተለመደ ሁኔታ ደራሲው በ1988 ዓ.ም. አድራሻው ስለጠፋበት ወንድሙ፣ ያፋልጉኝ ማስታወቂያ ያወጣ ሲሆን፣ በ39 ብር ለገበያ መቅረቡም ታውቋል፡፡

.....ስንታየሁ መልካ እባላለሁ፡፡ የመጣሁት በሲዳማ ዞን ከሸበዲኖ ወረዳ ነው፡፡ ሙያዬም ክሊኒካል ነርስ ነኝ፡፡ በስራዬ አንድ የማልረሳው አጋጣሚ አለኝ፡፡ ሴትየዋ ለሕክምና ስትመጣ እንግዴ ልጅ ከማህጸንዋ ጋር ተጣብቆ ነበር፡፡ ጊዜ ወስደን ብንጠብቅም ከማህጸን ለመላቀቅ አልቻለም፡፡ ስለዚህ ሴትየዋ እንዳትጎዳ በመፍራት ወደከፍተኛ ሐኪም ላክናት፡፡ ነገር ግን አሁን በስልጠና ላይ እንዳየሁት ከሆነ ለካስ ሴትየዋን በቀላሉ ማዳን ይቻል ነበር፡፡ ከዚህም በተጨማሪ ደም እየፈሰሳቸው የሚመጡ እናቶች ቢያጋጥሙን ጤና ጣብያ ላይ ምንም እርዳታ ለመስጠት ሳንሞክር እናስተላልፋለን፡፡ ነገር ግን ይህ ስልጠና ብዙ ነገር አስተምሮናል፡፡ ማከም የሚቻለውን ማከም...ማከም የማይቻል ከሆነ ግን በፍጥነት አላስፈላጊ መዘግየትን በማስወገድ ወደ ከፍተኛ ሕክምና ማስተላለፍ እንዳለብን በሚገባ ተረድተናል.....
                                                 -----///-----.
...ትእግስት ተሸመ እባላለሁ፡፡ ከጎርጂ ወረዳ ከጎርጂ ጤና ጣብያ ነው ለስልጠናው የመጣሁት፡፡ እኔ በሙያዬ ጤና መኮንን ነኝ፡፡ በሕክምናው ዘርፍ ከተሰ ማራሁ ወዲህ የማልረሳው አንድ አጋጣሚ አለኝ፡፡ እርጉዝዋ ሴት ለሕክምና ስትመጣ እትብቱ ከልጁ ቀድሞ ወጥቶ ነበር፡፡ እንደዚህ ያለ አጋጣሚ ተከስቶ አይቼ ስለማላውቅ በጣም ነበር የደነገጥኩት፡፡ አብረውኝ የነበሩትም ለነገሩ እንግዳ በመሆናቸው አማራጭ አልነበረንም። ወደከፍተኛ ሕክምና ላክናት፡፡ ነገር ግን እስከዛሬ የሚቆጨኝ ...እኛጋ በነ በረችበት ሰአት የልጁዋ የልብ ትርታ ይደመጥ የነበረ ሲሆን ወደተላለፈችበት ጤና ተቋም እስክትደርስ ግን ትርታው አልቀጠለም፡፡ በመሀከል ልጁዋን አጥታለች፡፡ ልጁን ያጣ ችው ይህች ሴት ብቻ ሳትሆን እንደዜጋ እንዲሁም እንደባለሙያ እኛም ነን ያጣነው፡፡ እናም እስከዛሬ ድረስ ይቆጨኛል፡፡ አሁን ግን ይህንን ስልጠና በማግኘታችን የምንች ለውን በፍጥነት መርዳት የማንችለውም ከሆነ አላስፈላጊ መዘግየትን በማስወገድ በፍጥነት ሌላ እርዳታ እንዲ ያገኙ ማድረግ እንዳለብን በሚገባ አውቄአለሁ፡፡ ቀደም ሲል በትምህርት ላይ እያለሁ የተወሰነ እውቀት ቢኖረኝም ተግባራዊ ሁኔታውን ግን በደንብ አላውቀውም ነበር፡፡ አሁን ግን በሚገባ ለመስራት ዝግጁ ነኝ፡፡
                                                 ----////----
ከላይ ያነበባችሁት WATCH (women ande their children health) ማለትም የሴቶችና ሕጻናትን ጤንነት መጠበቅ በሚል ትርጉዋሜ የተሰየመው በጎ አድራጊ ድርጅት ከኢሶግ እና ከፕላን ኢንተርናሽናል ኢትዮጵያ ጋር በመተባበር ከሚሰራባቸው አካባቢዎች በሲዳማ ዞን ሐዋሳ ከተማ በመሰጠት ያለውን ስልጠና በተከታተልንበት ወቅት ያነጋገርናቸው ሰልጣኞችን ምላሽ ነው፡፡ በማስከተል የምናስነብባችሁ የዞኑን የጤና መምሪያ ኃላፊ የአቶ በድሉ ባዴጎን ማብራሪያ ነው፡፡
አቶ በድሉ ባዴጎ የሲዳማ ዞን ጤና መምሪያ ኃላፊ እንዳብራሩት ከምእተ አመቱ የልማት ግቦች ከስምንቱ ውስጥ ሶስቱ በጤናው ዘርፍ ያተኮሩ ናቸው፡፡
1. የእናቶችን ሞት በ3/4ኛ መቀነስ ፣
2. የህጻናትን ሞት በ2/3ኛ መቀነስ፣
3. ዋና ዋና ተላላፊ በሽታዎችን...ወባ ኤችአይቪ ኤይድስ ቲቪ...መከላከል ናቸው፡፡
ከላይ ከተጠቀሱት ውስጥ የሲዳማ ዞን ከ WATCH እና ከፕላን ኢንተርናሽናል ኢትዮጵያ እንዲሁም ከኢሶግ ጋር እየሰራ ያለው የእናቶችና ሕጻናትን ሞት መቀነስ በሚያስችለው ዙሪያ ነው፡፡
የእናቶችንና የህጻናቱን ጤና ለመጠበቅ ከሚያስችሉት መንገዶች ዋነኛው እናቶች በጤና ተቋም መውለድ መቻላቸው ነው፡፡ እናቶች ወደ ጤና ተቋም ለመውለድ ሲመጡ በሰለጠነና ብቃት ባለው የጤና ባለሙያ እንዲወልዱ እና መድሀኒትና የህክምና አገልግሎት መስጫው በተቋሙ በተሟላ ሁኔታ እንዲገኝ ማድረግ አስፈላጊ ነው፡፡ ስለዚህም በሁሉም የጤና ተቋማት ለተሰማሩ ባለሙያዎች መሰረታዊ ድንገተኛ የእናቶችና የጨቅላ ሕጻናትን እርዳታና እንክብካቤ በሚመለከት ስልጠና ሲሰጣቸው በዛ ረገድ እናቶችም ጨቅላ ሕጻናቱም ተጠቃሚ ይሆናሉ የሚል እምነት አለ፡፡ በእርግጥ ከምእተ አመቱ የልማት ግብ ጋር በተያያዘ ከዚህም በተጨማሪ የጨቅላ ሕጻናቱ ክትባት የሚያገኙበት እንዲሁም እናቶች የቤተሰብ እቅድ ዘዴ፣ በእርግዝና ወቅት ቢያንስ እስከ አራተኛ ዙር የሐኪም ክትትል ማድረግ፣ በምጥ ሰአት በጤና ተቋም በመቅረብ እንዲወ ልዱ የማድረግ ስራ በስፋት እየተሰራ ይገኛል፡፡ በሲዳማ ዞን በተለይም በ2005 ዓ/ም እናቶች በቤታቸው የመውለድ እርምጃ እንዳይወስዱ ለማድረግ የሚያስችል አሰራር ተዘርግቶ እርጉዝ የሆኑ እናቶችን በየቀበሌው በመመዝገብ እና መድረክ በመፍጠር ውይይት እንዲያደርጉ ሁኔታ ዎች ተመቻችተወ ተግባራዊ ተደርገዋል፡፡ በጤና ባለሙያ ምርመራ በማድረግም የሚወል ዱበ ትን ጊዜ እንዲያውቁት የማድረግ ስራ በመሰራት ላይ ስለሆነ በዚህም መነሻነት ምጥ ሲጀምራ ቸው ጊዜ ሳይፈጁ በአቅራቢያቸው ወደሚገኘው ጤና ተቋም በመሄድ መውለድ የሚችሉበት ሁኔታ ተመቻችቶአል፡፡ በዚህም ብዙ እናቶች ወደጤና ተቋም በመቅረብ በመውለድ ላይ መሆናቸውን ለማወቅ ተችሎአል፡፡
አቶ በድሉ የባለሙያዎችን የሙያ ብቃት በሚመለከት የአሰራር ለውጥ መኖሩን ገልጸዋል፡፡ የትምህርት ማስረጃ ብቻ በቂ ባለመሆኑ ተጨማሪ የብቃት ማረጋገጫ ፈተና ከ2003/ ዓ/ም ወዲህ በመሰጠት ላይ ስለሆነ ብቃቱን በማረጋገጥ ወደሚቀጥለው ትምህርት እንዲገቡ በመደረግ ላይ ናቸው። በተለይም በጤና ሙያው ዘርፍ ለመቀጠርም ይህንን ፈተና ተፈትነው ሲያልፉ ብቻ ወደ ዘርፉ ይገባሉ፡፡ ወደህክምናው ዘርፍ የተሰማሩትን ባለሙያዎች በስልጠና ማገዝ ተገቢ በመሆኑም የተለያዩ ድርጅቶች ስልጠና ሲሰጡ ዞኑም ተገቢውን ባለሙያ በመምረጥ ለተሻለ እውቀት ስልጠና እንዲያገኙ ሁኔታዎችን ያመቻቻል፡፡ በዚህም አሰራር የእናቶችንና የጨቅላ ሕጻናቶቻቸውን ሞት እንቀንሳለን የሚል እምነት አለን ብለዋል፡፡
በ WATCH ድጋፍ በኢትዮጵያ የጽንስና ማህጸን ሕክምና ባለሙያዎች ማህበር አማካኝነት በዞኑ ሶስት ወረዳዎች ላይ ለተወሰኑ ባለሙያዎች የሚሰጠውን ስልጠና በሚ መለከትም እንዳብራሩት ስልጠናዎች የሚካሄዱት በመንግስት ፕሮግራም እየታገዙ ነው፡፡ መንግስት በራሱም ፕሮግራም ይሁን በተባባሪ አካላት አማካኝት ስልጠናው በሁሉም የዞኑ የህክምና ተቋማት ላሉ ባለሙያዎች እንዲሰጡ የበኩሉን ያደርጋል፡፡ በመሆኑም በየጤና ጣብያው አፋጣኝ የእናቶችንና የጨቅላ ሕጻናቶችን ጤንነት በመንከባከብ ረገድ ለሁሉም ባለሙያ ስልጠናው እንዲደርስ ለማድረግ መንግስት የራሱን አቅጣጫ አስቀምጦ እየሰራ ይገኛል፡፡ መንግስት የሚችለውን እያሰለጠነ ሲሆን መንግስት የማይደርስበትን ደግሞ ከተባባሪ ድርጅቶች ጋር በመተባበር ይሰራል፡፡
አቶ በድሉ ባዴጎ እንደገለጹት በ WATCH ድጋፍ በፕላን ኢንተርናሽናል ኢትዮጵያ እና በኢሶግ ትብብር በዞኑ በመሰጠት ላይ ያለው ስልጠና ወሳኝነት አለው፡፡ መሰረታዊ ድንገተኛ የእናቶችና የጨቅላ ሕጻናቶች እንክብካቤ ስልጠና በየጤና ጣቢያው እንዲሰጥ እና የሰለጠኑ ሰዎች ህብረተሰቡን እንዲያገለግሉ ማድረግ ዞኑ በእቅድ የያዘው አሰራር ነው፡፡ ስለዚህም ይህንን አቅጣጫ በመከተል በዞኑ በሶስት ወረዳዎች ላይ ስልጠናን ለመስጠት የተደረገውን ስምምነት ከግብ ለማድረስ ዞኑ አብሮ በመስራት ላይ ይገኛል፡፡ በዚህም መሰረት በሸበዲኖ፣ ቦና እና ጉርቺ ወረዳዎች ላይ በሁለት ዙር ለአስራ ስምንት ቀን ስልጠናው ተሰጥቶአል፡፡ ሰልጣኞች ከስልጠ ናው ያገኙትን እውቀት በሶስት ሆስፒታሎች በቀንና በማታው ክፍለ ጊዜ በመመደብ በተግባር እንዲተረጉሙ በመደረጉ ይበልጡኑ እውቀታቸውን የሚያዳብሩበት አጋጣሚ ተከስቶአል፡፡ እያንዳንዱ ሰልጣኝ ቢያንስ ቢያንስ እስከ አምስት እናት የማዋለድ ስራ እንዲሰሩና ምናልባትም የማዋለድ ተግባሩ አስቸጋሪ ሁኔታዎችንም ጭምር እንዲመለከቱ ስለሚያስችላቸው ወደመጡበት የህክምና ተቋም ሲመለሱ ችግር አገልግሎቱን በብቃት ለመስጠት ያስችላል፡፡ ስልጠናው የሚሰጠው በብሄራዊ ደረጃ በተነደፈው ጋይድ ላይን መሰረት ስለሆነ ባለሙያዎችን ብቁ እንደሚያደርጋቸው እሙን ነው፡፡
በስልጠናው ላይ የተሳተፉት ባለሙያዎች ወደስራ መስካቸው ሲመለሱ በህክምና መገልገያ እና በመድሀኒት አቅርቦት በኩል የአሰራር ችግር እንዳይገጥማቸው ማድረግን በተመለከተ አቶ በደሉ ባዴጎ የሲዳማ ዞን ጤና መምሪያ ኃላፊ እንደገለጹት በኢፊድሪ ጤና ጥበቃ ሚኒስ..ር በኩል በየጤና ጣቢያው እናቶችንና ጨቅላ ሕጻናቶችን በማከም ረገድ ምን መሳሪያዎች እና መድሀኒቶች አስፈላጊ እንደሆኑ አስቀድሞ ይታወቃል፡፡ በእርግጥ ግዢው በውጭ ምንዛሪ በመሆኑና ዋጋውም በጣም ውድ ስለሆነ የሚያስፈልጉ ቁሳቁሶችን በአንድ ጊዜ ማሟላት እንደማይቻል እሙን ነው፡፡ ቢሆንም ግን የህክምና መሳሪያዎቹን ደረጃ በደረጃ ለወረዳዎች እያቀረበ ሲሆን በሂደት ይሟላል የሚል ተስፋ አለ፡፡ ከዚህ በተጨማሪ ፕላን ኢንተርናሽናል ኢትዮጵያ ከ WATCH ጋር ተባባሮ ለስድስት ጤና ጣቢያዎች የህክምና መገልገያ እቃዎችን ገዝቶ ያቀረበ ሲሆን ይህ ድጋፍ በዚህ ይቆማል የሚል ግምት የለም። በቀጣይም ሌሎች ፕሮጀክቶችን በመቅረጽ ለተቀሩት ጤና ጣቢያዎች አስፈላጊውን ድጋፍ እንደሚያደርጉ በመነጋገር ላይ እንገኛለን፡፡ ነገር ግን ሁኔታውን መንግስት በፕሮራም ይዞ አስፈላጊውን እያደረገ ስለሆነ በወደፊት አሰራሩ ጤና ተቋማቱ በቂ በሆነ የሕክምና መገልገያ ቁሳቁስ ስራቸውን መስራት የሚችሉበት ሁኔታ ይኖራል የሚል እምነት አለ ብለዋል አቶ በደሉ ማዴጎ በማጠቃለያ ሀሳባቸው፡፡

“ለግብረሰዶማውያን ግን ቅጣታቸው ሰይፍ ነው!”
“ልጃገረዷን በግድ ቢይዛት አፍንጫውን ይፎንኑት፡፡ ለእርሷም ከገንዘቡ ሲሶውን ይስጧት። አስራ ሶስት ዓመት ሳይሆናት አስቀድሞ ልጃገረዲቱን የያዛትን ሰው አፍንጫውን ይፎንኑት፡፡ ከገንዘቡም እኩሌታውን ለእርሷ ይስጧት፡፡”
ይህ ሕግ ነው፤ ሴቶችን ከእንስሳዊ ጥቃት ለመታደግ ከ570 ዓመት በፊት የተደነገገ፡፡ ዘመኑ የአገራችን ሥነ ጽሑፍ አብቦበት እንደነበረ የሚነገርለት ነው - የአፄ ዘርዓ ያዕቆብ (1434-1468) ዘመነ መንግስት፡፡ ለሥነ ጽሑፉ መዳበር ትልቁን ድርሻ የሚይዙት ከጉንዳንጉዶ ገዳም የተነሱት የአባ እስጢፋኖስና ደቀመዛሙርታቸው አዲስ ሃሳብ ማቀንቀን ነው፡፡ መነኮሳቱ ለሚያነሱት አዲስ ነገረ መለኮት መልስ ለመስጠት ሲባል በርካታ መጻሕፍት በንጉሱ እና በተቃራኒው ወይም በነባሩ አስተሳሰብ መመራትን በሚሹ መነኮሳት ይጻፉ ነበር፡፡
“ፍትሐ ነገሥት” የተባለው የሕግ መጽሐፍ ሥራ ላይ የዋለውም ከዚያ የፍትጊያ ዘመን ጀምሮ ነው፡፡ በ1923 ዓ.ም በወጣው ሕገ መንግሥት እስከተተካ ድረስም ለአራት መቶ ሰማንያ ዘጠኝ ዓመታት መንግሥትና ሃይማኖት/በተለይ የኦርቶዶክስ ተዋሕዶ እምነት/ በተግባር ሲያውሉት ቆይተዋል፡፡
ዛሬ “የሕግ ትምህርት ቤት” እንደሚባለው ድሮ ፍትሐ ነገሥት ራሱን ችሎ ወይም ከትርጓሜ መጻሕፍት ጋር በአንድ ጉባኤ ትምህርቱ ሲሰጥ ቆይቷል፡፡ ፍትሐ ነገሥት የተማሩት ሊቃውንትም ከነገሥታቱ የፍርድ አደባባይ ላይ በመገኘት ነገሥታቱ በፍትሐ ነገሥቱ ህግጋት መሠረት የፍርድ ሥራቸውን እንዲያከናውኑ ያግዙ ነበር፡፡
የፍትሐ ነገሥቱ ድንጋጌዎች የተመሠረቱት በብሉይና አዲስ ኪዳን መጻሕፍት ላይ ሲሆን በተለይ አስገድዶ መድፈርንና ግብረ ሰዶማዊነትን በተመለከተ የሚያስገርሙና ጠንከር ያሉ ድንጋጌዎችን ይዞ ይገኛል፡፡ በነገራችን ላይ ኢትዮጵያ የሕግ ቅርስ ካላቸው ጥቂት የዓለማችን አገሮች አንዷ እንድትሆንም አስችሏታል፡፡ ህጉ (ፍትሐ ነገሥት) በተለይ ጥቃት ለሚደርስባቸው ሴቶች ተገቢ መፍትሔ እንደነበረው ከተደነገጉት አናቅጽ መረዳት ይቻላል፡፡
“ያልተነካ ግልግል ያውቃል” እንደሚባለው ምን አልባት “ሕጉ የሚጥለው ቅጣት ጠንካራ ነው፤ ኋላቀር ነው” ሊባል ይችላል፡፡ ግን በወቅቱ ልጃገረድ ደፋሪዎች አፍንጫቸው ይፎነን (ይቆረጥ) ነበር። ቅጣቱ የሚያሳየው ጭካኔን ሳይሆን ወንጀሉ ምን ያህል ትኩረት እንደተሰጠው ነው። እናም በወቅቱ አፍንጫ ፎናና (ቆራጣ) ሰው ከታየ ለምን እንደተቆረጠ ምክንያቱ ግልጽ ነበር፡፡ ወንጀል አድራጊውም ከደረሰበት የአካል ጉዳት ይልቅ የማህበረሰቡ መጠቋቆሚያ መሆኑ እያሳፈረው ዕድሜውን በሰቀቀን መግፋት ግድ ይሆንበታል። አካሉን ከማጣቱ ሌላ ግማሽ ሃብቱ በተደፋሪዋ ስለሚወረስበት የሰራው ወንጀል የአካል ብቻ ሳይሆን የምጣኔ ሃብት ጣጣ ስለሚያስከትልበት ውርደቱና የሞራል ስብራቱ ከተደፋሪዋ በላይ ይሆናል፡፡ ቅድመ 1923 የነበሩ ነገሥታት ይህን ህግ በተገቢው መንገድ ስለሚተረጉሙ ከመሰል ድርጊት ሁለመናን መሰብሰብ ግዴታ ነበር፡፡
በፍትሐ ነገሠቱ አንቀጽ 48 ላይ የተደነገገው ይህ ጠንካራ ሕግ፣ ዛሬ ተግባራዊ ቢሆን ስንቱ አፍንጫ ፎናና ይሆን ነበር? ምክንያቱም በ1949 ዓ.ም ወጥቶ ከ48 ዓመታት በኋላ በ1997 ዓ.ም የተሻሻለው የወንጀል ህጋችን አንቀጽ 620 (1) ለተመሳሳይ ጥፋት የሚጥለው ቅጣት ከአምስት እስከ አስራ አምስት ዓመት የሚደርስ እስራት ነው፡፡
የተጠቂዋ ዕድሜ ከ18 ዓመት በታች ከሆነ፣ በተከሳሹ ጥበቃ ወይም ቁጥጥር ሥር የምትገኝ ወይም የእሱ ጥገኛ ከሆነች፤ ወይም በዕድሜ መግፋት፣ በህመም፣ ወይም በሌላ ምክንያት የድርጊቱን ምንነት በውል ለይታ በማታውቅ ሴት ላይ ሲሆን፤ የተደፈረችው ከአንድ በላይ በሆኑ ወንዶች ሲሆን፣ ቅጣቱ ከአምስት እስከ 20 ዓመት በሚደርስ እሥራት እንዲሆን ይደነግጋል (620፡2) እድሜዋ ከ13 ዓመት በታች በሆነ ሕጻን ላይ ለሚፈፀም ጥቃትም ህጉ ከ15-25 ዓመት እስራት ቅጣት ይደነግጋል፡፡
አስገድዶ መድፈሩ ከባድ የአካል ወይም የአዕምሮ ጉዳትን ወይም ሞትን ያስከተለ ከሆነ ግን “ቅጣቱ የዕድሜ ልክ እሥራት ይሆናል (620፡3)” ይላል፡፡ ግን እድሜ ልክ እስራት 25 ዓመት ሲሆን ጥፋተኛው 20 ዓመት ከታሰረ አምስቱን ዓመት ሳይቀጣ በአመክሮ ይለቀቃል፡፡
ይህ ታላቁ የዘመናችን ቅጣት ነው፡፡ ቅጣቱ ከባድ ይመስላል፤ ግን ከፍትሐ ነገሥቱ ድንጋጌ አንቀጽ 48 ጋር ሲገናዘብ ደካማ ነው፡፡ ምክንያቱም ደፋሪው የህጻናትን ህይወት በዘላቂነት የተጐዳ ስለሚያደርገው፣ የፈፀመው ድርጊትም እንስሳዊ ስለሆነ ጠንከር ያለ ቅጣት ይገባው ይመስለኛል፡፡
በመገናኛ ብዙሃን በተደጋጋሚ የምንሰማውና የምንናበው ድርጊት በእጅጉ ይሰቀጥጣል፡፡ የ60 ዓመት አዛውንት የሶስት ዓመት ሕፃን መድፈሩ፣ ወይም የ20 ዓመት ወጣት የ70 ዓመት ባልቴት ማዋረዱ፤ ሶስት ወይም አራት ወሮበሎች አንዲትን ደካማ ሴት በህብረት ማጥቃታቸው ወዘተ እጅግ በጣም አሳፋሪም ነውረኛም ድርጊት ነው፡፡ ታዲያ ለእንዲህ ዓይነቱ ነውረኛና አደገኛ ድርጊት ቆንጠጥ የሚያደርግ ቅጣት ካልተጣለ እንዴት ነው “የጾታ ዕኩልነት ተከብሯል” የሚባለው?
አፍንጫ የመፎነኑ ቅጣት የሚያሳየን ትልቅ ቁምነገር በቀልን አይደለም፤ ይልቁንም በተጠቂዋ ሥነልቡና እና ዘላቂ ህይወት ላይ ምን ያህል ከባድ ጉዳት እንደደረሰ ነው፡፡ ለዚህም ነው በአጥቂው ላይ ቋሚ ምልክትና የገንዘብ ቅጣት ይወሰን የነበረው፡፡ የአሁኑ የወንጀል ህጋችን አጥፊውን ይቀጣል እንጂ ተበዳዩ እንዲካስ አያደርግም፡፡ ፍትሐ ነገሥት ግን አጥፊው ከባድ ቅጣት ተቀጥቶም ተበዳዩን ይክሳል፡፡
ሕጉ የወንጀል ብቻ ሳይሆን የፍትሐ ብሔርን ድርሻም ጨምሮ ይሰራ ነበር፡፡ ዛሬም ጥቃት የደረሰባት ሴት የሞራል ካሣ ልትጠይቅ ትችላለች። ግን ከሚጠብቃት ውጣ ውረድ ሌላ ገንዘቡም ደካማ ነው፡፡ ፍትሐ ነገሥቱ የደፋሪዎችን አፍንጫ ከመፎነን የሚያስጥል ሌላ ድንጋጌም አለው። እንዲህ ይላል “በፈቃድዋ ወይም ያለፈቃድዋ ወላጆቿ ሳያውቁ ከልጃገረድ ጋር የተገናኘ ሊያገባት የሚወድ ቢሆን ለወላጆቿ ፈቃዱን ይፈጽሙለት ዘንድ ምርጫ ይገባቸዋል፡፡ ከወላጆቿ አንዱ እንቢ ቢል የገሰሳት ሰው ቢቻለው ባለፀጋም ቢሆን ምዝን ወርቅ ይስጣት፤ በሁሉም ችግረኛ ቢሆን ገርፈው ራሱን ላጭተው ይስደዱት” (ገፅ 419) ይላል፡፡
ይህን ድርጊት በፈፀመው ሰው ላይ ህጉ ጥብቅ እርምጃ እንዳይወሰድበት የሚያደርገው ዓላማውን በመደገፍ ነው፡፡ ጋብቻ ትልቅ ማህበራዊ ተቋም ነው፡፡ እንደተቋምነቱም ህጉ ጥበቃ ያደርግለታል። ለዚህም ነው ክብረ ንጽህናዋን የገሰሰ ወንድ መጀመሪያ ድርጊቱን ለምን ዓላማ እንደፈፀመው መታወቅ የሚገባው፡፡ ጉልበት ስላለው ብቻ ከደፈረ ቅጣቱ ያው የአፍንጫ መፎነን ነው፤ ለጋብቻ ዓላማ ግን ቅጣቱ ቀላል እንዲሆን የታሰበበት ይመስላል፡፡ በተለይ ከወላጆቿ አንዱ ካልተስማማ እና አጥፊው ድሃ ከሆነ ቅጣቱም ቀለል እንዲል ተደርጓል፡፡ ሃብታም ከሆነ ግን ጋብቻውም የማይፈቀድለት ከሆነ ምዝን ወርቅ የመክፈል ግዴታ ተጥሎበታል፡፡
ምዝን ወርቅ አሁን በምናውቀው ሚዛንና መመዘኛ የሚታሰብ አልነበረም፤ የክብደቱ መለኪያ ድቡልቡል ድንጋይ ነበር፡፡ እናም ከድንጋዩ ክብደት ጋር የሚመዝን ወርቅ መክፈል ይጠበቅበታል ማለት ነው፡፡ ይህን ማድረግ ካልቻለ የገንዘቡን (የሃብቱን) ዕኩሌታ እንዲሰጣት ይገደዳል፡፡
ከዚህ አንፃር ሲታሰብም ፍትሐ ነገሥት የሴቶችን መብት በማስከበር ረገድ ትልቅ ትኩረት ይሰጥ እንደነበር እንገነዘባለን፡፡ ዛሬ በትዳር አጋራቸው ወይም በፍቅረኛቸው ገላ ላይ አሲድ እየረጩ፣ በጩቤ ዓይናቸውን እየጐለጐሉ፤ ወይም በአደባባይ በጥይት እየደበደቡ፣ ወይም በልጆቿ ፊት የእናታቸውን አንገት በቢላዋ እንደ ዶሮ የሚቀነጥሱ፣ ወዘተ ጨካኞችና ነውረኞች እንደ አሸን ሲፈሉ “ምናለ በፍትሐ ነገሥት ዘመን ተፈጥረን ቢሆን ኖሮ” ያሰኛል፡፡
ሌላውና ጠንካራው የፍትሐ ነገሥት ድንጋጌ በግብረሰዶማውያን ላይ ይጥል የነበረው ቅጣት ነው፡፡ “ግብረሰዶም የሚሰሩ ሰዎች ለአድራጊውና ለተደራጊው ቅጣታቸው ሰይፍ ነው፡፡ ተደራጊው 12 ዓመት ያልሞላው ቢሆን የዘመኑ ማነስ ከቅጣት ያድነዋል” (ገፅ 421) ይላል፡፡ ዛሬ ላይ ይህ ሕግ በአገራችን እየተሰራበት ቢሆን ኖሮ የስንቱ ብላሽ አንገት ለሰይፍ ይዳረግ እንደነበር ሳስበው “ምን አለ መንግሥት ይህን የፍርድ መጽሐፍ ቢያነብበውና የአገሪቱ የወንጀል ሕግ አካል ቢያደርገው” የሚል ብርቱ ምኞት ያድርብኛል፡፡ ይህ ደግሞ ያለምክንያት አይደለም፤ ጨካኝ ባህርይ ኖሮኝም አይደለም፡፡ ምንም በማያውቁ ህጻናት ላይ የሚፈፀመውን ዘግናኝ ድርጊት ስለምሰማ ነው፡፡ በቅርቡ እንኳ ጉዳያቸው በፍርድ ቤት በመታየት ላይ ያለ የስድስት መምህራን ድርጊት ይህን አይነት ቅጣት እንድመኝ ገፋፍቶኛል። ልጅን ያህል ታላቅ አደራ ተሰጥቷቸው በትክክልና በስርዓት አስተምረው መላክ ሲገባቸው አንድን ህፃን ለስድስት መድፈር በእርግጥስ በሰይፍ ሊያስቀጣ የሚችል እጅግ ከባድ ወንጀል አይደለም?
ለእንዲህ ዓይነቶቹ ነውረኛ ግለሰቦች የልብ ልብ የሰጣቸው የወንጀል ህጋችን መላላት ይመስለኛል፤ ጉዳዩን በተመለከተ የወጣው ድንጋጌ አንቀጽ 631 (1) እንዲህ ይላል፡፡
“ማንም ሰው ከእርሱ ጋር አንድ አይነት ጾታ ባለውና ለአካለ መጠን ባልደረሰ ልጅ ላይ የግብረ ሰዶም ጥቃት የፈፀመ እንደሆነ ሀ) የተበዳዩ ዕድሜ አስራ ሶስት ዓመት ሆኖ አስራ ስምንት ዓመት ያልሞላው ሲሆን ከሶስት ዓመት እስከ አስራ አምስት ዓመት በሚደርስ ጽኑዕ እሥራት፤ ለ) የተበዳዩ ዕድሜ ከ13 ዓመት በታች ሲሆን ከ15-25 ዓመት በሚደርስ ጽኑዕ እሥራት ይቀጣል፡፡”
ሴት ለሴት የሚደረግ ግብረሰዶማዊነትንም ህጉ እንደወንዶች ባይሆንም በወንጀል ፈጻሚዎች ላይ የተለያየ የቅጣት ዕርከን ደንግጓል፡፡ ግን እንደ ፍትሐ ነገሥቱ አስተማሪ አይደለም፡፡ በ1977 ዓ.ም ወሎ ክፍለ ሃገር በደረሰው ከባድ ድርቅ ምክንያት ወላጆቻቸውን በረሃብ የተነጠቁ ህፃናትን ለመርዳት “ጃሪ የህፃናት መንደር” በውጭ አገር ሰዎች ቢመሰረትም ምንም በማያውቁ ምስኪን ህጻናት ላይ ከፍተኛ የሆነ ግብረሰዶማዊ ጥቃት ሲደርስባቸው ነበር፡፡ ከጊዜ በኋላ ጥቃቱን ራሳቸው ተጐጂዎቹ ቢያጋልጡም ከፊሉ ወንጀለኞች አገር ጥለው ሲወጡ የተያዘው አንድ ግለሰብ ግን በስምንት ዓመት እስር ብቻ እንደተቀጣ አስታውሳለሁ፡፡
በርካታ ህፃናት (ያውም ወላጆቻቸውን በጠኔ የተነጠቁ) ላይ አስነዋሪ ድርጊት የፈፀመ ወንጀለኛ ሰይፍ አይገባውም ነበር? እርግጥ ነው ዳኞች ህጉ ከሚደነግገው በላይ አልፈው ሊቀጡ ስልጣን የላቸውም፡፡ የሴቶችንና የህፃናትን ጥቃት ለመከላከል ግን ዛሬም ፍትሐ ነገሥት ያሻን ይመስለኛል፤ እንወያይ!

ከአዘጋጁ፡- ከዚህ በታች የቀረበው ፅሁፍ ከዶ/ር መረራ ጉዲና የኢትዮጵያ ፖለቲካ ምስቅልቅል ጉዞና የህይወቴ ትዝታዎች መፅሃፍ አለፍ አለፍ ተብሎ የተወሰደ ሲሆን መፅሃፉን ያላገኙ አንባቢያን መጠነኛ ግንዛቤ እንዲያገኙ በሚል ያወጣነው ነው፡፡
ምዕራፍ 11፡ የ2002 ምርጫና አዳዲስ የኢህአዴግ ሴራዎች
በሀገር ውስጥም ከሀገር ውጪም የብዙ ሰዎች ዓይን የተተከለው በ1997ቱ ምርጫ ላይ ነው። እስከ 1997ቱ ምርጫ ድረስ ደግሞ የብዙዎች የፖለቲካ እይታ የተሰራው በተጨናገፈው የ1966ቱ አብዮት ላይ ነበር፡፡ የ1997ቱ ምርጫ ለሁለተኛ ጊዜ የትውልድን ቀልብ ስቦ አልፎአል፡፡ ህዝቡን ከዛ አላቆ ወደፊት እንዲመለከት ለማድረግ ቀላል አልሆነም፡፡ በምርጫ ውጤት ተደናግጦ የነበረው ኢህአዴግም አስተማማኝ ምርኩዜ ነው በሚለው ጠመንጃ ስር መደበቁን መርጧል፡፡ ተቃዋሚውም ድርጅት ከመፈልፈልና ከመከፋፈል በሽታው አልዳነም። በተለይ አንባቢ ልብ እንዲልልኝ የምፈልገው፣ ተቃዋሚው በ1997ቱም ሆነ ዛሬ ሰፊ ህዝባዊ ድጋፍ (popular support) አለው። ዛሬም ከአንድ ወር ባነሰ እንቅስቃሴ ኢህአዴግን ኮርቶ ማሸነፍ ይችላል። የኢህአዴግ ባለስልጣናትም በህዝብ እውነተኛ ድጋፍ ሳይሆን የሀገሪቷን ፀጥታ ኃይል ምርኩዝ አድርገው እንደሚኖሩ ልቦናቸው ያውቃል፡፡ ተቃዋሚው በ1997ቱም ሆነ ዛሬም በቂ የተደራጀ ድጋፍ (organized support) የለውም፡፡ ደጋግሜ ለማሳየት እንደሞከርኩት ይህ ክፍተት ካልተደፈነ በስተቀር ሁሉም ነገሮች በጎ ፈቃድ እስከምን ድረስ ድረስ እንደሆነ በ2002ቱ ምርጫ በሚገባ አይተናል። ስለሆነም፣የተቃዋሚዎች አጣዳፊ ተግባር መሆን ያለበት ክፍተቱን በመድፈን አቅም ፈጥሮ መንቀሳቀስ ብቻ ነው፡፡
እስከሚገባኝ ድረስ የሀገራችን ፖለቲካ አንድ ወሳኝ እርምጃ ወደፊት ሊሄድ የሚችለው ሁሉም ከራሱ የህልም ዓለም በመውጣት፣ ዲሞክራቲክ ኢትዮጵያን ለመፍጠር ዋነኛ አጀንዳ ላይ መረባረብ ነው፡፡ ይህን ለማድረግ ደግሞ፣ በአንድ በኩል መገንጠልን እንደዋነኛ የፖለቲካ አጀንዳ ማራመድንና በሌላ በኩል ደግሞ “ኢትዮጵያ እምዬ ምኒሊክ በፈጠሯት መልኳ ትኑር” የሚሉትን ሁለቱን የሀገራችንን የፖለቲካ ጫፎች በማቀራረብ በመሃል መንገድ ላይ ወርቃማ አማካይ (the golden mean) መፍጠር ያስፈልጋል፡፡ ከታሪክ ጣጣችን የሚመነጩ ልዩነቶች በአንድ ጀንበር ካልተፈቱ ብሎ የሙጥኝ ማለት የዲሞክራቲክ ኢትዮጵያን መወለድ ማዘግየትና የገዢው ፓርቲ የከፋፍለህ ግዛ ሴራ ሰለባ ከመሆን ያለፈ ምንም ፋይዳ የለውም። የአንዳንዶች ህልም እስኪሟላ የጋራ ህልም እንዳይሳካ ማጨናገፍ፣ከራስ ህልም ጋር እየዋዠቁ ከመጓዝ ያለፈ የፖለቲካ ፋይዳ የለውም፡፡ ያለፉት የአርባ ዓመታት ታሪካችንም የሚያረጋግጥው ይህንኑ ሃቅ ነው፡፡
ምርጫ 97 እና 2002
በሁሉም መንገድ የ2002 ምርጫ የ1997ቱን አይመስልም፡፡ ኢህአዴግ የ1997ቱ ጎርፍ ተመልሶ እንዳይመጣበት በዓለም ሊኖሩ የሚችሉ ሁሉም ምርጫን የማዛባት ታክቲኮችን ቀምሞ ነበር የጠበቀን፡፡ ከሁሉም በላይ የ1997ቱን የሕዝብ ጎርፍ የቀሰቀሰውን የቀጥታ ስርጭት ክርክር እንዳይኖር አድርጓል፡፡ ጥቂት የተፈቀዱ ክርክሮችም የተደረጉት በተመልካች አልባ ስቱዲዮ በቀጥታ የማይሰራጩ ነበሩ፡፡ በቴሌቪዥንና ሬድዮ እንዲነበብ የሚደረጉ የሳንሱር መቀስን ማለፍ ነበረባቸው፡፡ ህዝባዊ ስብሰባዎችም በብዙ መንገዶች ተተብትበው እንዳይካሄዱ ተደርገዋል፡፡ የተካሄዱትም የ1997ቱን ጎርፍ የሚመስሉ በጥቂት ቦታዎች ብቻ ነበር፡፡ ለአብነት መኪናችንን እንዲሰብሩ የንብ ምክንቶች (ንብ ኢህአዴግ የምርጫ ምልክት ነው) የያዙ ወጣቶች በብዙ ቦታዎች ተሰማርተው መንገድ ይዘጉብን ነበር፡፡ አንዳንድ ቦታዎች እስታዲየሞች ተፈቅዶልን ቁልፍ የያዙ ዘበኞች እንዲሰወሩ ተደርገዋል፡፡ እዚህ ላይ አንባቢው የተሻለ ሥዕል እንዲኖረው ትንሽ ልዘርዝር፡፡
በኢትዮጵያ ታሪክ ውስጥ ባልታዬ መንገድ በተደረገው የ1997ቱ ክርክር ውስጥ በተደጋጋሚ ተሳትፎ የነበረኝ ሰው፣በ2002ቱ ምርጫ የተሳተፍኩት አንድ ጊዜ ብቻ ነበር፡፡ እሷም በተደረገችው በጠባብ ስቱዲዮ ያለተመልካች ስትሆን፣ኢህአዴግ ጋዜጠኛ ጠያቂ ሆኖ፣አጠቃላይ ሁኔታውን በተቆጣጠረበት መንገድ ነው፡፡ የቀጥታ ስርጭቱን ስለከለከሉ ፕሮግራሞች ተቆራርጠው ይተላለፉ ነበር፡፡ ኢህአዴግ በፈለገበት ሰዓትና መንገድ ብቻ ነበር የሚቀርቡት፡፡ ንፅፅር ካስፈለገ ጣሊያን የአድዋን ሽንፈትዋን ለመቀበል የቻለችውን ሁሉ ተዘጋጅታ ከ40 ሰዓት በኋላ እንደመጣች ሁሉ ኢህአዴግም የ1997ቱን ሽንፈቱን ለመቀበል ሊያደርግ የሚችለውን ሁሉ አድርጎ ነበር ተዘጋጅቶ የመጣው፡፡ በእንግሊዝ ዲፕሎማቶች አቀናባሪነት (ሴራም ለማለት ይቻላል) አቶ ሃይሉ ሻውልም የፈረሙት ስነ-ምግባር ተብዬው ምን ያክል እንደጎዳን ያወቅሁት ለቅስቀሳ መስክ በወጣሁ ጊዜ ነበር፡፡ “እዚህ ቤተክርስቲያን አለ፣ቅስቀሳ ክልክል ነው፤ እዛ መስጊድ አለ መቀስቀስ አይቻልም፤ ዛሬ ገበያ ነው ቅስቀሳ አይፈቀድም፤ እዚህ ትምህርት ቤት አለ፤ መቀስቀስ ፈፅሞ የተከለከለ ነው” እየተባለ እንቅስቃሴዎቻችንን ገደቡ፡፡ ከሌሎቹ የመድረክ መሪዎች በተለየ መንገድ ለመንቀሳቀስ ስለሞከርኩ ኢህአዴግም እያንዳንዱን እንቅስቃሴዬን ለመቆጣጠር መንቀሳቀሱን ያወቅሁት ከውስጥ ከተገዙት አባሎቻችን፣ ሲፈን ጐንፋ የሚባል ወጣት በመጨረሻ ላይ ከያዘው ለየት ያለ የድምፅ መቅጃ መሣሪያ ጋር የተያዘ ጊዜ ነው፡፡ ይህን ልጅ ብጠረጥር በኦነግነት እንጅ በጭራሽ በመንግሥት ሰላይነት አልነበረም፡፡ ሲፈን እውነተኛ የኦሮሞ ልጅ ለመሆን ስሙን ወደ ኦሮሞ የቀየረና፣ አንድ ጊዜ ኦፒድኦ ብዙ የኦሮሞ ዩኒቨርስቲ ተማሪዎችን ጂማ ላይ ሰብስቦ የድርጅት አባል እንዲሆኑ የጠየቀ ጊዜ “ኦፒዲኦ ከመሆን እራሴን እሰቅላለሁ” ብሎ ገመድ ይዞ ሲሮጥ ተማሪዎች ተረባርበው እንዳስጣሉት መረጃው ስለነበረኝ፣ በፍጹም ለመንግስት ሰላይ ሆኖ ይሠራል ብዬ አልጠረጠርኩትም፡፡ ከነድምፅ መቅጃው እጅ ከፍንጅ ባይያዝ ኖሮ ሰው ሰላይ ነው ብሎ ቢነገረኝ አላምንም ነበር፡፡ ከመኢሶን ዘመን ጀምሮ በክህደት ባልደነግጥም፣ የዚህኛው ልጅ ትንሽ ገርሞኛል። ፖሊሶች ሊይዙት ሲሉ፣ የያዘውን ወረቀት አኝኮ ውጧል ተብሎ የሚወራለት አበራ የሚባል ዘመዱም እንዲሁ በቀላሉ ከድቶናል፡፡ የኦሮሞ ልጆች ለዓላማቸው ሳይሆን ለሆዳቸው ብለው ሕዝባቸውን ሲክዱ ከመናደድ ይልቅ በጣም ያሳዝነኛል፡፡ ሲፈን ጎንፋ የሚባለውን ልጅ ከኔ ጋር ለቅስቀሳ ወደ ወለጋ ስንሄድ፣ ቶኬ የምትባል የትውልድ አካባቢዬ ላይ ሆዱ እጅግ በጣም ገፍቶ እርጉዝ ሴት የመሰለ ሰው፣ “ኢህአዴግን ለልማት ምረጡ” የሚል መፈክር ይዞ ቆሞ አገኘነው፡፡ ሲፈን ቶሎ ብሎ የዚህን ሰው ያረገዘ ሆድ እያሳየ “የቶኬ ህዝብ በአንተ ሀብት የለማው አንተ ሳትሆን የእሱ ሆድ ነው” ማለቱንና የኢህአዴግ ካድሬዎች የሰበሰቡት ሕዝብ ጭምር ሲስቅበት፣ ሰውዬው አፍሮ ቦርጩንና የኢህአዴግን መፈክር ይዞ መሰወሩ ዛሬም ትዝ ይለኛል፡፡ ከዛን ጊዜ ጀምሮ ሲፈንን ባላየውም ሆዱ እንደዛ ሰው ለምቶ ይሆናል። እሱም የከዳን ከዛ ለተሻለ ዓላማ አይመስለኝም፡፡
“የሐረርጌ ህዝብ ልብ ከናንተ ጋር ነው”
…ከ1997ቱ ምርጫ ይልቅ በሰሜን ሸዋ/ስላሴ በ2002ቱ ምርጫ ብዛት ባላቸው ወረዳዎች ውስጥ ብንወዳደርም፣ እንቅስቃሴያችን ብዙ የተሻለ አልነበረም፡፡ መለስተኛ ሕዝባዊ ስብሰባዎችን ያደረግነው በኩዩና ወረጀርሶ (ጐኃጽዮን) ከተማ ብቻ ነበር፡፡ በቀሩት ከተሞች፣ እንደቡ አቦቴ የነጄኔራል ታደሰ ብሩ ወረዳ ጨምሮ በብዙ ቦታዎች ያደረግነው በጎዳና ላይ ቅስቀሳ ብቻ ነበር፡፡ የመንገድ ላይ ቅስቀሳውን ግን ብዙ ሠርተንበታል፡፡
ከሰላሌ ቀጥሎ ጉዞአችን ወደ አንዱና ትልቁ መሥመራችን የሐረርጌ መሥመር ነበር፡፡ በዚህ መሥመር፣ በሁለት ፓርላማ አባላት የሚመሩ ሁለት ቡድኖችን አስቀድመን አስመርተን ነበር፡፡ እኔ ተከትያቸው ስደርስ፣ በምዕራቡም፣ በምሥራቁም የ1997ቱ ምርጫን የመሰለ የሕዝብ ጐርፍ አልነበርም። ተወዳዳሪዎቻችንም ከጫት ያለፈ ዓላማ የነበራቸው አይመስልም፡፡ ከ90ሺ በላይ ሕዝብ ወጥቶ፣ እኔንም ሰዎች ተሸክመው መድረክ ላይ ያወጡበት የሐረር ከተማ ጭር ብላ ነበር የጠበቀችን፡፡ ሐሮማያ/ዓለማያ ዩኒቨርሲቲ አጠገብ በጠራነው ስብሰባ የዩኒቨርሲቲ ተማሪዎች እንኳ አልነበሩም፡፡ ስብሰባውን ለማዳመጥ ከመጡት ሰዎች የመንግሥት ቪዲዮ አንሺዎች ይበዙ ነበር፡፡ የነበረን ብቸኛ አማራጭ በጎዳና ላይ ሰፊ ቅሰቀሳ አድርገን ወደ ድሬዳዋ ማምራት ነው፡፡ የድሬዳዋ ከተማ የኦሮሚያ ክልልና የሱማሌ ክልል ካድሬዎች የሚራኮቱበት ቦታ ስለሆነችና በከተማው ላይ ስብሰባ የምናካሂድበት ቦታ ስለከለከሉን በሦስት ላንድክሩዘሮች የመንገድ ላይ ቅስቀሳችንን አድርገን ወደጨለንቆ ጉዞአችንን ቀጠልን፡፡ ጨለንቆ ላይ የነበረው አህመድ ነጃሽ የሚባለው ተወዳዳሪያችን የጃራ አባ ገዳ የቅርብ ዘመድ የሆነ ሰው ስለሆነ እራሱን ችሎ ለመንቀሳቀስ የሚችል ነበር፡፡ ከዛ ሁለት ቀን በፊት ደደር ላይ ከባድ ዝናብ ዘንቦ ስብሰባ እንደከለከለን፣ ጨለንቆ ላይም ከለከለን። ተፈጥሮም ከነዚህ ሰዎች ጋር ተባብሮብናል ብለን ወደ ጭሮ አመራን፡፡ ጭሮ ላይ ኦፒዲኦ መሆናቸውን ባይረሱም፣ ቢራ የጋበዙን የኦፒዲኦ ልጆችን አገኘን፡፡ ገለምሶና ጭሮ ላይ መለስተኛ ስብሰባዎችን አድርገን ወደ ሸገራችን ተመለስን፡፡ እንደ ሐረር ከተማው፣ ጭሮም ላይ የ1997ቱን ስብሰባ የመሰለ ነገር ማካሄዱ አልተሳካልንም፡፡ የ1997ቱ ምርጫ ላይ አግኝታኝ የነበረች ልጅ “የህዝብ ብዛቱን አይተህ አትዘን፤ የሀረርጌ ህዝብ ልብ ከእናንተ ጋር ነው” አለችኝ፡፡ በዚሁ ጥሩ ማፅናኛ የሐረርጌን ህዝብንና ምድር ተሰናብተን ጉዟችንን ወደ ሸዋ ቀጠልን፡፡

በጥንት ጊዜ አንድ ሰው ወደ ጐረቤቱ ማሳዎች ተደብቆ በመዝለቅ እህል አጭዶ ሊሰርቅና ሊወስድ ወሰነ፡፡ “ከሦስቱም ማሳዎች ትንሽ…ትንሽ አጭጄ ብወስድ አይታወቅም፡፡” በማለት ራሱን አሳመነ፡፡ “ለእኔ ግን ከሁሉም ማሳዎች የምሰበስበው ብዙ ይሆንልኛል፤” በማለት አሰበ፡፡
ስለዚህ ሰውየው ቀኑ ሲጨላልምና ደመናው ሲከብድ ያሰበውን ስርቆት ተግባራዊ ለማድረግ ተነሳ፡፡ ደመናው ጨረቃዋን ሲሸፍናትና አካባቢው ሲልም ሴት ልጁን ይዞ፣ ከቤቱ ወጣና ተሹለክልኮ ከማሳዎቹ ዘንድ ደረሰ፡፡
“ትሰሚያለሽ…ልጄ…የሆነ ሰው ካየኝ ንገሪኝ፡፡ እዚህ ጋ በትጋት ቁሚና ጠብቂ” በማለት ትንሿን ልጁን አዘዛትና እርሱ ወደ አንዱ ማሳ እየተንሿከከ ገባ፡፡
ሰውየው በመጀመሪያው ማሳ ገብቶ እያጨደ ስርቆቱን ተያያዘው፡፡ ብዙም ሳይቆይ ልጅቷ “አባቴ ኧረ እየታየህ ነው!” አለችው፡፡
ቆም ብሎ ዙሪያውን ሲመለከት ምንም ነገር የለም፡፡ የቻለውን ያህል አጭዶና ተሸክሞ ወደ ሁለኛው ማሳ ገባና ያጭድ ጀመር፡፡
“አባቴ አሁን ታይተሃል” በማለት ልጁ ተናገረች፡፡ ማጨዱን አቁሞ፣ አሁንም አካባቢውን ማተረ። ምንም ነገር ስላልታየው አጭዶ የሠረቀውን ሰበሰበና ወደ ሦስተኛው ማሳ ገባ፡፡ እዚያም ማጨድ እንደጀመረ፣ “አባቴ ኧረ እያዩህ ነው ታይተሃል!” እያለች ልጅቷ ጮኸች፡፡
ሌባው ሰውዬ አካባቢውን ቢቃኝም የሚታየው ነገር ስለሌለ ስርቆቱን ጨርሶ የሰበሰበውን አስሮ ተሸከመ፡፡ ወደ ልጅቷ ተጠግቶ “ማንም ሰው ሳያየኝ “አዩህ” እያልሽ ለምን ታስጨንቂኛለሽ?!” በማለት እየተናደደ ተቆጣት፡፡
“አባቴ፤ አንተ ግራና ቀኝ፣ ፊትና ኋላ እያየህ፣ ማንም የለም ትላለህ፡፡ የታየኸው ወይም ያየህ ከላይ ነበር፡፡ አንተ እኮ ወደ ሰማይ ቀና አላልክም” አለችው፡፡
* * *
አንታይም ብለን ያደረግነው ሁሉ የማታ ማታ የሚያየውን እጅ ላይ እንደሚጥለን አንርሳ፡፡ በዚያኛው ዘን ያደረግነው ወደዚህኛው ዘመን፣ በዚህኛው ዘመን ተደብቀን ሳይነቃብን ያለፍነው፤ በመጪው ዘመን ሊከሰትብንና ከላይ የሚያይ እንደሚያየን ልብ እንበል፡፡ የምናደርገው ክፉ ሥራ ሁሉ እንደጥቁር ጥላ ይከተለናል፡፡ ህሊናችንን ያመናል፡፡ እንቅልፍ እንደነሳን ይኖራል፡፡ “ሞት ላይቀር ማንቋረር” እንደሚባለው ነው፡፡ ከዚህም ከዚያም በዘረፍነው ገንዘብ ፎቅ ስንገነባ፣ ውድ ውድ መኪና ስንገነባ፣ ሰፋፊ ቢዝነስ ስንከፍት ወዘተ፤ ሌሎች ኑሯቸው እየቆረቆዘ፣ ሀገሪቱ ከነግ ሠርክ ቁልቁል እየወረደች መሄዷን የሚያይ ዐይን አለ፡፡
ከላይ ጂ ቤኔት “የማታየው ያይሃል” ብሎ የፃፈውና ደራሲ ገ/ክርስቶስ “ደወል” በሚለው መጽሐፉ ተርጉሞ ያስቀመጠው ተረት የሚነግረን ይሄንኑ ነው፡፡ እንደ ሌባው አባት ሴት ልጅ “ኧረ እየታየህ ነው” የሚል የማስጠንቀቂያ ደወል የሚያንቃጭል አመራር ያስፈልገናል፡፡
ጤናችን በታወከበት፣ ትምህርታችን እየተዳቀቀ በሄደበት፣ ኪነጥበባችን ከእጅ ወደ አፍ በሆነበት፣ መቻቻላችን አጠያያቂ በሆነበት፣ ዲሞክራሲያችን አገም ጠቀም እየሆነ በሄደበት፣ መልካም አስተዳደራችን የብልጭ ድርግም ባህሪ በሚያሳይበት፣ ሰው ከዕለት ወደዕለት ራስ ወዳድነቱ ከሀገሩ ጥቅም እያየለ በተጓዘበት፣ ግብረ ገብነት የክፉ ቀን እርግማን በመሰለበት፤ የችግሮቻችን መፍትሔዎች “ጡቷን ስትሸፍን ታፋዋ ታየ፤ ታፋዋን ስትሸፍን ጡቷ ታየ” እየሆኑ ባሉበት፤ ሁኔታ ውስጥ የጉዳያችንን ጥልቀት አስተውለን የበለጠ ጥንቃቄ፣ የበለጠ ትጋት፣ የበለጠ ትግል እናደርግ ዘንድ የማስጠንቀቂያ ደወል ያሻናል፡፡ ይህን እንደበለጠ የጥረት መቀስቀሻ እንጂ እንደመርዶ ወይም እንደሟርት አንየው፡፡ እልህ ኖሮን እንነሳሳ!!
በእርግጥ ፒተር ዳያማንዲስ እንደሚለን፤ “የሚደማ ጉዳይ መሪ ዜና ይሆናል” የሚለው ጥንት ስለጋዜጦች የተነገረ ዕውነት ቢሆንም፤ ዛሬም ይሰራል፡፡
(If it bleeds, it leads እንዲሉ ፈረንጆቹ፡፡) “ዋሽንግተን ፖስት” ጋዜጣን አንሱና አሉታዊና አዎንታዊ፣ ደግና ክፉ፣ ዜናዎችን አወዳድሩ፡፡
ከዘጠና በመቶ በላይ ሐተታዎቹ ክፉ ወሬን የሚተርኩ ናቸው፡፡ በአጭሩ ደግ ደጉ ዜና ትኩረታችንን አይስብም፡፡ ምክንያቱም “አሚግዳላ” የተባለው የአንጐላችን ክፍል ሁሌም የሚያስፈራ’ንን ነገር ለመፈለግ ይገፋፋናል፡፡ ባጭሩ አንጐላችን አንዴ ክፉ ወሬን ፍለጋ ከተሰማራ፤ ክፉ ወሬ ያገኛል” ይኸው ፀሐፊ አጠንክሮና አበክሮ እንዲህ ይለናል፡፡ “የዛሬ ጊዜ አደጋዎች ከሞላ ጐደል የምናልባቴ ጉዳዮች ናቸው (Probabilistic)፡፡ ኢኮኖሚ ባፍንጫው ወይም ባፍጢሙ ሊደፋ ይችላል (nose-dive)፡፡ በማናቸውም ሰዓት የአሸባሪዎች ጥቃት ሊከሰት ይችላል፡፡ የሚገርመው ፍርሃትንና ቁጣን የሚቆጣጠረው የአንጐላችን ክፍል (አሚግደላ) በሁለቱ መካከል ያለውን ልዩነት ላያውቅ ይችላል፡፡”
አዎንታዊ እንዳንሆን ሦስት ቅጣቶች አሉብን 1ኛ/ የአዕምሮአችን የማጣሪያ ነገረ-ሥራ ክፉ ክፉውን የሚመኝ ሆነ 2ኛ/ ሚዲያ ተነባቢ ለመሆን ክፉ ክፉውን ዜና መረጠ፡፡ 3ኛ/ ሳይንቲስቶችም የማንወጣበት ገደል ውስጥ ነን ማለታቸው ብቻ ሳይሆን ለመውጣት ፈቃደ ልቦናው የለንም ማለታቸው ነው፡፡
ዓለም፤ የሚያስፈራ አደጋ እያሸተተና የማያስተማምን መሆኑን፤ ፀሐፍት እየነገሩን ነው፡፡ ይህንን እንግዲህ ወደ ሀገራችን ሁኔታ መመንዘር ነው፡፡ እንደ ነጋዴ ስንጥቅ እያተረፍን “ባመጣሁበት ውሰደው” ባንልም፤ አደጋውን በሙስናው፣ በኢፍትሐዊነቱ፣ በአስተዳደር ጉድለቱ፣ በኢኮኖሚ ዝቅጠቱና በመቻቻል መመናመኑ ወዘተ ውስጥ አስተውሎ ሁሌ ንቁ ሆኖ ማየት ነው፡፡
ምዕራቦቹ የሚጠጣ ንፁህ ውሃና የሚተነፈስ ንፁህ አየር እየጠፋ ነው እያሉ ሥጋቱ ሊገላቸው ነው። እኛ ጥያቄው ከነመኖሩንም አናውቅም፡፡
እነሱ እየተቆጣጠሩትም ፍርሃቱ ሊገላቸው ደርሷል፡፡ እኛ እርምጃቸውንም ከጉዳይ አልጣፍነውም። እነሱ “ዓለም ወዴት እየሄደች ነው” ብለው ተጨናንቀው ሊሞቱ ነው፡፡ እኛ የዘረፍነውን ዘርፈን “እቺ አገር ወዴት እየሄደች ነው” እያልን በማላገጥ ላይ ነን! በዚህ ዓመት ምህረቱን ያምጣልን (If it bleeds it leads እንዳንል ይጠብቀን፡፡) ክፉ ወሬ ቀዳሚ ርዕሰ-ጉዳይ እንዳይሆን እንፀልይ፡፡
“በድህነቷ ላይ አገውኛ ጨመረችበት” የሚለው የትግሪኛ ተረት ያሳስባል፡፡ የሀገራችን አንዱ ችግር የጉዳዮች የአንድ ሰሞን ዘመቻ
መሆን ነው፡፡ ጨበጥነው፤ ተቆጣጠርነው ስንል፤ ተመልሶ እዛው ይዘፈቃል፡፡
ቢያንስ ለዘንድሮው ዓመት፤
“ጅግራ ያዝ፣ ሩጫ ከፈለክ ልቀቃት፤
ሥጋ ከፈለክ እረዳት” የሚለውን ተረት ልብ እንድንል ልብና ልቦና ይስጠን!!.

አንድነት ለዲሞክራሲ እና ለፍትህ ፓርቲ በነገው ዕለት በአዲስ አበባ ለማካሄድ አቅዶት የነበረውን ሰላማዊ ሰልፍ ለመስከረም 19 ማዛወሩን የፓርቲው ዋና ፀሃፊ አቶ ዳንኤል ተፈራ ገለፁ፡፡
ፓርቲው “የሚሊዮኖች ድምፅ ለነፃነት” በሚል መሪ ቃል ለሶስት ወራት ሲያደርግ የቆየውን የተቃውሞ ሰልፍ ማጠናቀቂያ በነገው ዕለት በአዲስ አበባ ለማድረግ አቅዶ የነበረ ሲሆን ከመስተዳደሩ ጋር ባደረጉት ውይይት ሰላማዊ ሰልፉን ለመስከረም 19 ለማዛወር ስምምነት ላይ መደረሱን አስታውቋል፡፡ ፓርቲው እስካሁን በተለያዩ ክልሎች ባካሄዳቸው ሰላማዊ ሰልፎች ላይ በራሪ ወረቀቶችና ፖስተሮች እንዳይበትኑና እንዳይለጠፉ እንዲሁም ቅስቀሳ እንዳያካሂዱ ጫና ይደረግባቸው እንደነበር የጠቆሙት የፓርቲው ዋና ፀሃፊ፤ እንዲህ ያሉ ችግሮች እንደማይደርስባቸው ከመስተዳደሩ ጋር ባደረጉት ውይይት እንደተገለፀላቸው ተናግረዋል፡፡
መስተዳደሩ እስከ መስከረም 16 ድረስ ምንም ዓይነት ሰልፍ ማድረግ እንደማይቻል የገለፀላቸው መሆኑን የተናገሩት አቶ ዳንኤል፤ ለዚህ ምክንያቱም ተማሪዎች ወደ ትምህርት ቤት የሚሄዱበት፣ የበዓል ወቅት በመሆኑና ለባቡር ዝርጋታ ተብሎ የተከለለው አጥር መነሳት ስላለበት እንደሆነ መስተዳደሩ ገልፆልናል ብለዋል፡፡ ፓርቲው ምክንያቱን ተቀብሎ የሰላማዊ ሰልፉን ቀን እንደለወጠና ከመስተዳደሩ ሰላማዊ ሰልፉ መፈቀዱን የሚገልፅ ደብዳቤ መቀበሉን ዋና ፀሃፊው ገልፀዋል፡፡
ቀኑ መቀየሩ ለእኛም ጥቅም አለው ያሉት አቶ ዳንኤል፤ ፖስተር ለመለጠፍ እና ፍላየር ለመበተን ጊዜ ያስፈልገን ነበር፤ ጊዜው መራዘሙ ይህንን በስፋት እንድናከናውን ያግዘናል ብለዋል። መስከረም 19 ቀን የሚደረገውን ሰላማዊ ሰልፍ የፓርቲው ሊ/መንበር ዶ/ር ነጋሶ ጊዳዳ እንደሚመሩትም አክለው ገልፀዋል - አቶ ዳንኤል።

“ሁዋዌ ኢትዮጵያ” በአዲስ ዓመት ዕለት ለክብረ የአረጋውያን ግብረ ሠናይ ድርጅት የተለያዩ ቁሳቁስ ስጦታ ያበረከተ ሲሆን የምሳም ግብዣ አድርጓል፡፡
ሁዋዌ፣ ያበረከተው ቁሳቁስ ትልቅ የልብስ ማጠቢያ ማሽን፣ የውሃ ማጣሪያ፣ ፍራሾች፣ ብርድልብሶችና የምግብ እህሎች ሲሆኑ፣ ጠቅላላ 60ሺህ ብር ግምት እንዳላቸው ታውቋል፡፡
ስጦታውን ለማዕከሉ መሥራችና ዳይሬክተር ለወ/ሮ ወርቅነሽ ሙንኤ ያስረከቡት የ “ሁዋዌ ኢትዮጵያ” ዋና ሥራ አስፈጻሚ ሚ/ር ቶኒ ዱዋን ባደረጉት ንግግር፤ በዚህ ልዩ ዕለት ከአረጋውያን አባቶቻችንና እናቶቻችን እንዲሁም ከማዕከሉ ሠራተኞች ጋር ተጋርተን የተመገብነው ምሳ የበዓል ስሜት መፍጠሩን እርግጠኛ ነኝ ብለዋል፡፡
ወ/ሮ ወርቅነሽ በዚሁ ጊዜ ባደረጉት ንግግር፤ ክብረ የአረጋውያን ምግባረ ሰናይ ድርጅትን ከስድስት ዓመት በፊት በቤተሰባቸው በጀት መጀመራቸው ጠቅሰው በአሁኑ ሰዓት 14 ሴትና 24 ወንድ አረጋውያንን በቀን ሦስት ጊዜ እያበሉ፣ እያለበሱና ንጽህናቸውን እየጠበቁ በመንከባከብ ላይ መሆናቸውን እየተንከባከቡ መሆኑን ገልፀዋል።
በማኅበረሰብ አቀፍ ፕሮግራማቸው ደግሞ፣ የአቅመ ደካሞችን ቤቶች ማደሳቸውን፣ የመሥራት አቅም ላላቸው ሴቶች ከ100 እስከ 150 ብር የገንዘብ ድጐማ በመስጠት ገቢያቸውን ከፍ እንዲያደርጉ መርዳታቸውን ጠቅሰው፣ በዚህ ፕሮግራም እስከ አሁን ድረስ 716 አረጋውያንን መርዳታቸውን አስታውቀዋል፡፡
የአዲስ አበባ መስተዳድር ለአረጋውያን መርጃ መሬት በነፃ ስለሰጣቸው አመስግነው፣ በቦታው ላይ 200 አረጋውያንን መያዝ የሚችል መኖሪያ፣ ሆስፒታል፣ እንግዳ ማረፊያ፣ የስብሰባ አዳራሽና የገቢ መፍጠሪያ ማዕከል እየገነቡ መሆኑን ጠቅሰው፣ አቅሙ ያለው ሁሉ ለግንባታው ድጋፍ እንዲያደርግላቸው ጠይቀዋል፡፡ “ሁዋዌ ኢትዮጵያ” በቴሌኮሙኒኬሽን ዘርፍ የተሰማራ የቻይና ኩባንያ መሆኑ ታውቋል፡፡

የአዲስ ዓመትን በዓል ምክንያት በማድረግ ዜቲኢ ኮርፖሬሽን በአዲስ አበባ የተለያዩ ክፍለከተሞች ለሚገኙ 70 ችግረኛ ቤተሰቦች የአዲስ ዓመት ድጋፍ አበረከተ፡፡
ባለፈው ማክሰኞ በአዲስ ዓመት ዋዜማ ዜድቲኤ ባደረገው ድጋፍ ለእያንዳንዱ ቤተሰብ አንድ እሽግ ደብተርና አምስት ኪሎ ስጋ የሰጠ ሲሆን በዕለቱ ህፃናትና ቤተሰቦች በኮርፖሬሽኑ ድጋፍ መደሰታቸውን ተናግረዋል፡፡
የዜቲኢ ሥራ አስኪያጅ ሚ/ር ሃን ኤችአር ድጋፉን አስመልክተው ሲናገሩ፤ “ዜቲኢ በመሰረተ ልማት አቅርቦት ስራ ላይ የተሰማራ ኩባንያ ብቻ ሳይሆን፤ ከማህበረሰቡ ጋር በጥብቅ የተቆራኘና የህዝቦችን አቅም በማጐልበት የሚያምን ነው” በማለት ኩባንያው ለመላው የኢትዮጵያ ህዝብ በደስታና በብልጽግና የተሞላ አዲስ ዓመት እንደሚመኝ ገልፀዋል ያሉት የጉለሌ ክፍለከተማ የሰራተኛ ቢሮ ሥራ አስኪያጅ ወይዘሮ መሰረት መንገሻ በበኩላቸው፤ “የዜቲኢን ድጋፍ በደስታ የምንቀበለው ነው፡፡” “ድጋፉ ኮርፖሬሽኑ ከኢትዮጵያ ህዝብ ጋር ያለውን ቅርርብና የህዝቡን አቅም በማጐልበት ረገድ የድርሻውን ለማበርከት ያለውን በጐ ፈቃድ ያሳያል።” ብለዋል - የዜቲኢ ድጋፍ ወደፊትም እንደሚቀጥል ያላቸውን ምኞት በመግለጽ፡፡

በሙዚቃው በመንቀሳቀስ የ11 ዓመታት ልምድ ያለው ዛዮን ሬብልሥ የሙዚቃ ባንድ የአዲስ አልበም “ፕሮቫ” ለአዲስ ዓመት ገበያ አቀረበ፡፡
ዛዮን ሬብልሥ የሙዚቃ ባንድ ለገበያ ያበቃው ፕሮቫ አልበም አራት ዘፈኖች ያሉት ሲሆን፤ ሚክሲንግና ማስተሩን ናቲ ሲምስ እንደሰራው ታውቋል፡፡ ከአራቱ ዘፈኖች የመጀመሪያው ‹‹አዲስ ዓመት›› የተባለው እና ጭብጡ አዲስ ተስፋ አዲስ ትውልድ በሚል የተሰራ ሲሆን ግጥምና ዜማ የሰሩት ዛዮን ሬብልሥ እና ናቲ ሲምስ ናቸው፡፡ ሁለተኛው ‹‹አፍሪካ›› በሚል ለአፍሪካ ህብረት 50ኛ ዓመት የወርቅ ኢዮቤልዮ የተሠራ ዘፈን ሲሆን፤ ግጥምና ዜማውን በመሥራት ዛዮን ሬብልሥ፣ ናቲ ሲምስ እና ዶቭ ቤንጂ ተሳትፈዋል፡፡
ሦስተኛው፤ ‹‹ላቭ ዊዝ ዋት ዊ ኒድ›› የተባለው ዘፈን ሲሆን፤ በዩቲዩውብ ተጭኖ ከሁለት ሺ አምስት መቶ በላይ ተመልካች ያገኘ ነው፡፡ በዚሁ ዘፈን ግጥምና ዜማ ሥራ ላይ ዛዮን ሬብልሥ፣ ናቲ ሲምስ እና ዶ/ር ቢ (ብሩክ ቦካ) ተሳትፈዋል፡፡ አራተኛው ዘፈን ‹‹ሳባዊት›› በሚል የተዘጋጀ ሲሆን፤ ግጥምና ዜማውን የሰሩት ዛዮን ሬብልሥ እና ናቲ ሲምስ ናቸው፡፡
ዛዮን ሬብልሥ የሙዚቃ ቡድን ሁሉንም ዓይነት ሙዚቃ ይሰራሉ፡፡ ሬብልስ የተባሉት ለአገራቸው መልካም እና ጥሩ ነገሮች በማሰብ ያዳበሩት የታጋይነት መንፈስ ሲሆን በተለይ በሬጌ ሙዚቃቸው የተካኑና ጥሩ መልዕክት እና አህጉራዊ አጀንዳ ያላቸው ዘፈኖችን በመሥራት ከፍተኛ ልምድ ያዳበሩ ናቸው፡፡ በዛዮን ሬብልሥ የሙዚቃ ቡድን ያሉት ዘፋኞች ውቅያኖስ ፍቅሩ፣ ቴዎድሮስ ኃይሌ እና ይስሃቅ ኤልያስ ናቸው፡፡ ባለፉት አምስት ዓመታት በአዲስ አበባ፣ በድሬደዋ እና በሀዋሣ በርካታ ተመልካች ያገኙ የሙዚቃ ዝግጅቶችን የሠራው ዛዮን ሬብልሥ የሙዚቃ ቡድን ከተለያዩ የሀገር ውስጥና የውጭ ሀገር አርቲስቶች ጋር በመሥራትም ይታወቃል፡፡
አራት ዘፈኖች ያሉበት የዛዮን ሬብልሥ ፕሮቫ አልበም በ2006 ዓ.ም ለገበያ የሚበቃው ሙሉ ዓልበም ማስተዋወቂያ እንደሆነ ተገልጿል፡፡

 

ወደ 20ኛው የዓለም ዋንጫ ለመብቃት ለጥሎ ማለፍ ምእራፍ ከደረሱ 10 የአፍሪካ ብሄራዊ ቡድኖች የኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን በእግር ኳስ ደረጃው፤ በፕሮፌሽናል ተጨዋቾቹ ብዛትና በዝውውር ገያው የዋጋ ተመኑ ዝቅተኛው መሆኑን ከትራንስፈርማርኬት ድረገፅ ያገኛናቸው አሃዛዊ መረጃዎች ያመለክታሉ፡፡
ኢትዮጵያ
የፊፋ ወርሃዊ ደረጃ- በዓለም 102 በአፍሪካ 27
የፕሮፌሽናል ተጨዋቾች ብዛት- 5
የዝውውር ገበያ ተመን -775ሺ ፓውንድ
የቡድኑ አማካይ እድሜ- 25.20
የኢንተርናሽናል ጨዋታዎች ብዛት- 321
አልጄርያ
የፊፋ ወርሃዊ ደረጃ- በዓለም 34 በአፍሪካ
የፕሮፌሽናል ተጨዋቾች ብዛት- 19
የዝውውር ገበያ ተመን -51.5 ሚሊዮን ፓውንድ
የቡድኑ አማካይ እድሜ- 26.8
የኢንተርናሽናል ጨዋታዎች ብዛት- 300
አይቬሪኮስት
የፊፋ ወርሃዊ ደረጃ- በዓለም 18 በአፍሪካ 1
የፕሮፌሽናል ተጨዋቾች ብዛት- 25
የዝውውር ገበያ ተመን -135 ሚሊዮን ፓውንድ
የቡድኑ አማካይ እድሜ- 26.9
የኢንተርናሽናል ጨዋታዎች ብዛት- 772
ናይጄርያ
የፊፋ ወርሃዊ ደረጃ- በዓለም 35 በአፍሪካ 5
የፕሮፌሽናል ተጨዋቾች ብዛት- 18
የዝውውር ገበያ ተመን -56 ሚሊዮን ፓውንድ
የቡድኑ አማካይ እድሜ- 24.10
የኢንተርናሽናል ጨዋታዎች ብዛት- 362
ጋና
የፊፋ ወርሃዊ ደረጃ- በዓለም 24 በአፍሪካ 2
የፕሮፌሽናል ተጨዋቾች ብዛት- 34
የዝውውር ገበያ ተመን -77 ሚሊዮን ፓውንድ
የቡድኑ አማካይ እድሜ- 25.20
የኢንተርናሽናል ጨዋታዎች ብዛት- 725
ኬፕቨርዴ
የፊፋ ወርሃዊ ደረጃ- በዓለም 36 በአፍሪካ 6
የፕሮፌሽናል ተጨዋቾች ብዛት- 25
የዝውውር ገበያ ተመን -16.5 ሚሊዮን ፓውንድ
የቡድኑ አማካይ እድሜ- 26.5
የኢንተርናሽናል ጨዋታዎች ብዛት- 244
ግብፅ
የፊፋ ወርሃዊ ደረጃ- በዓለም 61 በአፍሪካ 11
የፕሮፌሽናል ተጨዋቾች ብዛት- 11
የዝውውር ገበያ ተመን -29 ሚሊዮን ፓውንድ
የቡድኑ አማካይ እድሜ- 26.5
የኢንተርናሽናል ጨዋታዎች ብዛት- 880
ቡርኪናፋሶ
የፊፋ ወርሃዊ ደረጃ- በዓለም 48 በአፍሪካ 7
የፕሮፌሽናል ተጨዋቾች ብዛት- 26
የዝውውር ገበያ ተመን -235 ሚሊዮን ፓውንድ
የቡድኑ አማካይ እድሜ- 26.7
የኢንተርናሽናል ጨዋታዎች ብዛት- 535
ሴኔጋል
የፊፋ ወርሃዊ ደረጃ- በዓለም 78 በአፍሪካ 17
የፕሮፌሽናል ተጨዋቾች ብዛት- 26
የዝውውር ገበያ ተመን -97.5 ሚሊዮን ፓውንድ
የቡድኑ አማካይ እድሜ- 25.5
የኢንተርናሽናል ጨዋታዎች ብዛት- 247
ካሜሮን
የፊፋ ወርሃዊ ደረጃ- በዓለም 51 በአፍሪካ 8
የፕሮፌሽናል ተጨዋቾች ብዛት- 28
የዝውውር ገበያ ተመን -125 ሚሊዮን ፓውንድ
የቡድኑ አማካይ እድሜ- 26
የኢንተርናሽናል ጨዋታዎች ብዛት- 498

  ========

የኢትዮጵያ ብሔራዊ ቡድን ባለፉት ሁለት ዓመታት ከፍተኛ ስኬት በማግኘት በአገሪቱ እግር ኳስ ላይ መነቃቃትን ፈጥሯል፡፡ ዋልያዎቹ በሚል ስሙ የታወቀው ይህ የእግር ኳስ ትውልድ ለዓለም ዋንጫ ለማለፍ 180 ደቂቃዎች ቀርተውታል፡፡ ዋልያዎቹ ከ31 ዓመታት በኋላ ለአፍሪካ ዋንጫ በማለፍ በ29ኛው አፍሪካ ዋንጫ ለመሳተፍ በቅተዋል፡፡ በሚቀጥለው ዓመት ደግሞ በደቡብ አፍሪካ በሚስተናገደው የአፍሪካ አገራት ሻምፒዮንሺፕ “ቻን” ተሳታፊ ናቸው፡፡ በዋልያዎቹ አስደናቂ ጥረት 2005 ዓ.ም በኢትዮጵያ እግር ኳስ ታሪክ ትልቁ ስኬት እንዲመዘገብ ሆኗል፡፡ የዚህ ትውልድ የኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን ተጨዋቾች የአገሪቱን የእግር ኳስ ደረጃ ብቻ አላሻሻሉም፡፡ በኢትዮጵያ እግር ኳስ የፕሮፌሽናሊዝም ጉዞ ፈር ቀዳጅ ለውጦችን እየፈጠሩ ናቸው፡፡ ብዙዎቹ የዋልያዎቹ አባላት ባገኙት ውጤት ልክ በገንዘብ ሽልማት ከ300 እስከ 450ሺ ብር በመሰብሰብ የላባቸውን ዋጋ እያገኙ ነው፡፡ በፕሮፌሽናል ተጫዋችነት ወደ 6 የተለያዩ አገራት ወደ የሚገኙ ክለቦች በመሰማራት ከፍ ያለ ደሞዝና ጥቅም በማግኘትም በዝውውር ገበያው ተፈላጊነታቸው እየጨመረ የመጣ ነው፡፡ ለመሆኑ ዋልያዎቹ ባለፉት ሁለት ዓመታት ያሳለፉት የእግር ኳስ ገድል ምን መልክ ነበረው? በአፍሪካ ዋንጫ እና የማጣርያ ውድድሮች ምን ታሪክ ሠሩ? በዓለም ዋንጫ በሁለት ዙር ማጣርያዎች 8 ብሔራዊ ቡድኖችን ጥለው ያለፉበት ጉዞ ምን ይመስላል?
ከ31 ዓመታት በኋላ በአፍሪካ ዋንጫ
ዋልያዎቹ ከ31 ዓመታት በኋላ ኢትዮጵያን ወደመሠረተችው አህጉራዊ ውድድር በመመለስ ደቡብ አፍሪካ ላስተናገደችው ለ29ኛው የአፍሪካ ዋንጫ ያለፉት በቀላሉ አልነበረም፡፡ በመጀመርያ የማጣሪያ ምዕራፍ ከቤኒን ጋር በጥሎ ማለፍ ተደልድለው በሜዳቸው 0ለ0 ሲለያዩ፣ በአበበ ቢቂላ ስታድየም የተደረገው ጨዋታ ጐል ማግባት ያልተቻለበት መሆኑ በወቅቱ የነበሩትን ቤልጅማዊ ዋና አሰልጣኝ ቆም ሴንትፌንት እና ምክትላቸውን ሰውነት ቢሻው ያስተቸ ነው፡፡ በመልሱ ቤኒን ላይ ሲጫወቱ 1ለ1 አቻ ሆኑ፡፡ ጐሏን ያስቆጠረው አዳነ ግርማ ነበር፡፡ ስለሆነም ከሜዳ ውጭ ባገባ በሚለው የአሸናፊ መለያ ህግ ወደቀጣዩ ምእራፍ ተሸጋገሩ፡፡ወደ አፍሪካ ዋንጫ ወደየሚያሳልፈው የመጨረሻው ምእራፍ ማጣርያ የተገናኙት ከጐረቤት አገር ሱዳን ጋር ነበር፡፡ በመጀመሪያው ጨዋታ ዋልያዎቹ በሜዳቸው ሱዳንን 2ለ0 ነበር ያሸነፉት፡፡ በመልሱ ጨዋታ ካርቱም ላይ ሲገናኙ እጅግ አስጨናቂ በነበረበት ጨዋታ 5ለ3 ተሸነፉ፡፡ በአጠቃላይ የደርሶ መልስ ጨዋታዎቹ ውጤት 5ለ5 እኩል ሆነ፡፡ ለ29ኛው የአፍሪካ ዋንጫ የሚያልፈው ብሔራዊ ቡድን ከሜዳው ውጭ ብዙ ባገባ በሚለው ተለየ፡፡ በሁለቱ የአፍሪካ ዋንጫ ማጣርያዎች በዋልያዎቹ የተሰበረ መጥፎ ሪከርድ ነበር፡፡ ከሜዳ ውጭ ወሳኝ ጐሎችን በማግባት ውጤታማ መሆን ስለተቻለ ነው፡፡ በዚህም የኢትዮጵያ ብሔራዊ ቡድን ከ31 ዓመታት በኋላ በአፍሪካ ዋንጫ ለመሳተፍ በቃ፡፡ በ29ኛው የአፍሪካ ዋንጫ የኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን በምድብ 3 ከናይጀሪያ ከቡርኪናፋሶ እና ዛምቢያ ጋር ተመደበ፡፡ በመጀመርያ ጨዋታ ከዛምቢያ ጋር 1ለ1 አቻ ወጣ ከዚያም በሁለተኛ ጨዋታው በቡርኪናፋሶ 4ለ0 እንዲሁም በመጨረሻው የምድቡ ጨዋታ በናይጀሪያ 2ለ0 ተሸነፈ፡፡ በዚህ ውጤቱ መሰረትም በምድብ 3 የኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን ባስመዘገበው 1 ነጥብና 6 የግብ እዳ የመጨረሻ ደረጃ ይዞ ከአፍሪካ ዋንጫው በግዜ ተሰናበተ፡፡ ዋልያዎቹ በአፍሪካ ዋንጫ መሳተፋቸው ትልቅ ውጤት ነበረው፡፡ የመጀመርያው በደቡብ አፍሪካ የሚገኙ ስደተኛ ኢትዮጵያውያን ለውድድሩ ከፍተኛ ድምቀት በማላበስ ለዋልያዎቹ ያስገኙት ትኩረት ነው፡፡ በሌላ በኩል ብሔራዊ ቡድኑ በምድቡ የመክፈቻ ጨዋታ ከዛምቢያ 1ለ1 አቻ ሲለያይ ለኢትዮጵያ የተመዘገበችው የአዳነ ግርማ ብቸኛ ጐል በአፍሪካ ዋንጫ ውድድር ከ33 ዓመት በኋላ የተመዘገበች ነበረች፡፡ የዋልያዎቹ አባላት በደቡብ አፍሪካ፣ በሰሜን አፍሪካ፣ በምስራቅ አውሮፓ ክለቦች በመፈለግ የፕሮፌሽናል እግር ኳስ ጉዟቸው የተሟሟቀው በአፍሪካ ዋንጫ በነበራቸው ተሳትፎ ነው፡፡
በሁለት ዙር የዓለም ዋንጫ ማጣርያዎች
ለ20ኛው የዓለም ዋንጫ ለማለፍ የኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን ወደ ማጣርያ ሲገባ በመጀመሪያ ዙር ለጥሎ ማለፍ ጨዋታ የተደለደለው ከጐረቤት አገር ሶማሊያ ጋር ነበር፡፡ የመጀመሪያው ጨዋታ በጅቡቲ ሲደረግ ውጤቱ 0ለ0 ነበር፡፡ ይህ ውጤት ስፖርት አፍቃሪውን ተስፋ ለማስቆረጥ የተፈታተነ ነበር፡፡ በመልሱ ጨዋታ አዲስ አበባ ላይ 5ለ0 ሶማሊያን ያሸነፉን ዋልያዎች ወደ ሁለተኛው ዙር የምድብ ማጣርያ ምዕራፍ ተሸጋገሩ፡፡ የኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን በምድብ 1 ከደቡብ አፍሪካ፣ ከቦትስዋና እና ከመካከለኛው አፍሪካ ነበር የተደለደለው፡፡ በምድቡ የመጀመሪያ ጨዋታ በሩስተንበርግ ሮያል በፎኬንግ ስታድዬም ከደቡብ አፍሪካ ጋር 1ለ1 አቻ በመለያየት ጥሩ ጅማሬ አደረጉ፡፡ ከሜዳ ውጭ ደቡብ አፍሪካ ላይ ጐሉን ያስቆጠረው ሳላዲን ሰኢድ ነበር፡፡ በ2ኛው የምድብ ጨዋታ ዋልያዎቹ በአዲስ አበባ ስታድዬም መካከለኛው አፍሪካ ሪፖብሊካን በማስተናገድ 2ለ0 አሸንፈው ምድቡን በአንደኛነት መምራት ጀመሩ፡፡ በዚህ ጨዋታ ላይም ሁለቱንም ጐሎች ከመረብ ያዋሃደው ሳላዲን ሰኢድ ነው፡፡ ከዚያም በ3ኛው የምድብ ጨዋታ አዲስ አበባ ላይ ቦትስዋናን ገጠሙ፡፡ በጌታነህ ከበደ ጐል 1ለ0 በማሸነፍ መሪነታቸውን አጠናክረው ቀጠሉ፡፡ ከዚያ በኋላ በ4ኛው የምድብ ጨዋታ ከቦትስዋና ጋር ዋልያዎቹ በዋና ከተማዋ ጋብሮኒ ሎባታሴ ስታድዬም ተገናኝተው 2ለ1 ከሜዳ ውጭ አሸንፈው ነበር፡፡ አንዱን ጐል ሳላዲን፣ ሌላኛው ጌታነህ አስቆጥረዋል፡፡ በዚሁ ጨዋታ በሁለት ቢጫ ካርድ ቅጣቱ መሰለፍ ያልነበረበት ምን ያህል ተሾመ ተሰልፎ ነበር፡፡ ኢትዮጵያ በፊፋ ህገ ደንብ ተቀጪ ሆና 3 ነጥብ 3 ነጥብ ተቀነሰባትና ሙሉ ሶስት ነጥብ እና የ3ለ0 ውጤት ለቦትስዋና እንዲሰጥ ተወስኗል፡፡ ከዚያ አሳዛኝ ጥፋትና ቅጣት በፊት የምድቡ 4ኛ ጨዋታ አዲስ አበባ ላይ ከደቡብ አፍሪካ ጋር የተደረገው ነበር፡፡ ዋልያዎቹ በሜዳቸው ደቡብ አፍሪካን 2ለ1 አሸነፉ፡፡ 1 ጐል ጌታነህ ከበደ ሲያስቆጥር የማሸነፊያውን ጐል ደግሞ የደቡብ አፍሪካው ተጫዋች መረብ ላይ ያገባው ነበር፡፡ ይሁንና ከምድቡ በመሪነት ማለፉን ለማረጋገጥ የምድቡ የመጨረሻ ዙር ጨዋታዎች መጠበቅ ነበረባቸው፡፡ ባለፈው ቅዳሜ በኮንጎ ብራዛቪል የምድብ 1 የመጨረሻ ጨዋታቸውን ከሴንተራል አፍሪካ ሪፖብሊክ ጋር ተደረገ፡፡ በሳላዲን ሰኢድ እና በምንያህል ተሾመ ጐሎች 2ለ1 በማሸነፍ ምድብ 1 ላይ በመሪነት ጨረሱ፡፡
የኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን በምድብ 1 የደረጃ ሰንጠረዥ በ6 ጨዋታዎች ምንም ሳይሸነፍ በ1 ጨዋታ በቅጣት 3 ነጥብ ተቀንሶበት በ13 ነጥብና በ2 የግብ ክፍያ መሪ በመሆን ለቀጣዩ ምእራፍ በቅቷል፡፡ ዋልያዎቹ በምድብ ማጣርያውን ያለፉበት ሂደት አስደናቂ ልዩ የሚሆነው በተመሳሳይ የተሳትፎ ታሪክ ትልቁ ውጤት በመሆኑ ነው፡፡ ከቅድመ ማጣሪያው ከተነሱ ዝቅተኛ ደረጃ ያላቸው 24 ብሔራዊ ቡድኖች ለመጨረሻው የጥሎ ማለፍ ምዕራፍ የደረሰው የኢትዮጵያ ብሔራዊ ቡድን ብቻ መሆኑ ደግሞ ሌላው ስኬት ነው፡፡ እስከ ምድብ ማጣርያው በአጠቃላይ 8 ጨዋታዎችን አድርገዋል፡፡ 5 ጨዋታዎችን ድል አደረጉ፡፡ አራቱን በሜዳ አንዱን ከሜዳው ውጭ ነው፡፡ በ2 ጨዋታዎች አቻ ወጡ፡፡ ሁለቱንም ከሜዳ ውጭ ነበር፡፡ እንደ ሽንፈት የተቆጠረው ግጥሚያ ሁለት ቢጫ ካርድ ያየ ተጨዋች በመሰለፉ የኢትዮጵያ ብሔራዊ ቡድን በመጀመርያ 2ለ0 አሸንፎ ለቦትስዋና በቅጣት በፎርፌ 3ለ0 እንዲሸነፍ የተደረገበት ነው፡፡ በስምንቱ ጨዋታዎች በተጋጣሚዎቹ ላይ 13 ጎሎች ያስመዘገበው ብሄራዊ ቡድኑ የተቆጠረበት ግብ 6 ሲሆን በእያንዳንዱ ጨዋታ በአማካይ 1.63 ጎሎች እንደሚያገባ እና 0.75 ጎል ሊገባበት እንደሚችል የፊፋ ስታስቲካዊ ስሌት ያመለክታል፡፡ ከስምንቱ የዓለም ዋንጫ ማጣርያ ግጥሚያዎች ሁሉንም በመሰለፍ ለ709 ደቂቃዎች የተጫወተው አበባው ቡጣቆ ነው፡፡ ስዩም ተስፋዬ በ7 ጨዋታዎች ለ575 ደቂቃዎች በመሰለፍ ከፍተኛውን አስተዋፅኦ አድርጓል፡፡ ሳላሃዲን ሰኢድ በ6 ጨዋታዎች ለ540 ደቂቃዎች በመሰለፍ አራት ጎሎች ያገባ ሲሆን ሌሎቹ በ6 ጨዋታዎች ያገለገሉት 446 ደቂቃዎች ተሰልፎ ሁለት ያገባው ሽመልስ በቀለ እና ለ540 ደቂቃዎች የተጫወተው አምበሉ ደጉ ደበበ ናቸው፡፡ አይናለም ሃይሉ፤ አስራት መገርሳ፤ አዲስ ህንፃ እና ምንያህል ተሾመ እያንዳንዳቸው በ5 ጨዋታዎች ለብሄራዊ ቡድኑ በመሰለፍ ከ425 እስከ 450 ደቂቃዎች ግልጋሎት የሰጡ የዋልያዎቹ አባላት ናቸው፡፡
ለዓለም ዋንጫ 180 ደቂቃዎች ጉዳይ
ኢትዮጵያ ለዓለም ዋንጫ የመጨረሻ የጥሎ ማለፍ ማጣሪያ በመብቃቷ በውድድሩ የተሳትፎ ታሪክ ትልቅ ውጤት ሆኖ ተዘመግቧል፡፡ በታሪካዊው የጥሎ ማለፍ ምዕራፍ የኢትዮጵያ ብሔራዊ ቡድን ከአፍሪካ 10 ብሔራዊ ቡድኖች አንዱ ሆኗል፡፡ የ3ኛው ዙር ወደ ዓለም ዋንጫ የጥሎ ማለፍ ድልድል ለ10ሩ ብሔራዊ ቡድኖች የሚወጣው ከሳምንት በኋላ በካይሮ ሲሆን የኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን ከምዕራብና ከሰሜን አፍሪካ ብሔራዊ ቡድኖች የሚገናኝበት እድል ያመዝናል፡፡ ብራዚል በ2014 እኤአ በምታስተናግደው 20ኛው የዓለም ዋንጫ ለመሳተፍ በዓለም ዙርያ ከሚገኙ 6 ኮንፌደሬሽኖች የተውጣጡ 203 አገራት መካከል በተለያዩ የማጣርያ ምእራፎች ሲደረግ የቆየው ፉክክር 34 ወራትን አስቆጥሯል፡፡ ይሄው የማጣርያ ሂደት ሊጠናቀቅ 2 ወራት ቀርቶታል፡፡ በአዘጋጅነት ያለፈችውን ብራዚል ጨምሮ ጃፓን፤ አውስትራሊያ፤ ኢራንና ደቡብ ኮርያ ለ20ኛው ዓለም ዋንጫ ማለፋቸውን ያረጋገጡ ናቸው፡፡ በቀረው የ27 ብሄራዊ ቡድኖች የዓለም ዋንጫ የተሳትፎ ኮታ በስድስቱ ኮንፌደሬሽኖች 67 አገራት የማለፍ እድል እንደያዙ ናቸው፡፡ በዓለም ዋንጫ የተሳትፎ ኮታ መሰረት ለአፍሪካ ዞን የተሰጠው እድል ለ5 ብሄራዊ ቡድኖች ነው፡፡ እነዚህን 5 ብሄራዊ ቡድኖች ለመለየት በአፍሪካ ዞን የሚደረገው የመጨረሻ ጥሎ ማለፍ ምእራፍ ከ5 ሳምንት በኋላ በመጀመርያ ጨዋታዎች ይጀመራል፡፡
በአፍሪካ ዞን የምድብ ማጣርያ ከ10 ምድቦች በመሪነት ያለፉት 10 ቡድኖች ታውቀዋል፡፡ እነሱም ግብፅ፤ አልጄርያ፤ አይቬሪኮስት፤ ጋና፤ ኢትዮጵያ ፤ ኬፕቨርዴ፤ ጋና፤ ቡርኪናፋሶ፤ናይጄርያ፤ ሴኔጋል እና ካሜሮን ናቸው።
ከሳምንት በኋላ ለአስሩ ብሔራዊ ቡድኖች ወደ የዓለም ዋንጫ የጥሎ ማለፍ ጨዋታ ድልድል በካይሮ ከተማ ሲመጣ ከቀናት በኋላ በሚታወቀው የፊፋ ወርሃዊ የእግር ኳስ ደረጃ መሠረት ነው፡፡ በደረጃ ሰንጠረዥ ከፍተኛ እርከን ላይ የሚገኙ 5 ብሄራዊ ቡድኖች በአንድ የእጣ ማሰሮ ሌሎች ዝቅተኛ እርከን ላይ የሚገኙ ብሄራዊ ቡድኖች በሁለተኛ ማሰሮ እንዲቀመጡ ይደረጋል፡፡ በማሰሮ 1 አይቬሪኮስት፤ ጋና፤ አልጄርያ፤ ናይጄርያና ኬፕቨርዴ አይስላንድ እንዲሁም በማሰሮ 2 ቡርኪናፋሶ፤ ካሜሮን፤ ግብፅ፤ ሴኔጋል እና ኢትዮጵያ ሊቀመጡ ይችላሉ፡፡ በዚህ መሰረት የኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን ወደ የዓለም ዋንጫ በሚያሳልፈው ጥሎ ማለፍ ከአይቬሪኮስት፤ ከጋና፤ ከአልጄርያ፤ ከናይጄርያ ውይም ከኬፕቨርዴ አይስላንድ ጋር የሚገናኝበት ሁኔታ የሚፈጠር ይመስላል፡፡ በደርሶ መልስ የጥሎ ማለፍ ጨዋታዎች ላይ የማሸነፍ እድል ቡድኖች እኩል 50 በመቶ ይሆናል፡፡ በዓለም አቀፉ ‹አርኢቺ ስፖርት ሶከር ስታትስቲክስ ፋውንዴሽን› የመረጃ መዝገብ መሰረት የኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን በኢንተርናሽናል ጨዋታዎች ባለው ታሪክ መነሻነት የሚያገኘውን ውጤት ለመገመትም ይቻላል፡፡ ስለሆነም የኢትዮጵያ ብሔራዊ ቡድን በጥሎ ማለፍ ሊገናኛቸው ከሚችላቸው 9 ብሄራዊ ቡድኖች ጋር ያለው የማሸነፍ ስኬት በመቶኛ ሲሰላ የሚከተለውን ይመስላል፡፡ የኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን በግምታዊ የጥሎ ማለፍ የጨዋታ ድልድል ላይ በማሰሮ 1 ሲደለደል ከአልጄርያ ጋር 50 በመቶ፤ ከአይቬሪኮስት ጋር 33.33 በመቶ፤ ከናይጄርያ ጋር 16.67 በመቶ፤ ከጋና ጋር 50 በመቶ የማሸነፍ እድል ሲኖረው ከኬፕቨርዴ ጋር በታሪክ ተገናኝቶ ስለማያውቅ ለመገመት ያስቸግራል፡፡ በተቀረ የኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን አብሮ በማሰሮ 2 ለድልድል ከተመደበባቸው ቡድኖች ጋር የሚገናኙበት ሁኔታ ከተፈጠረ ከቡርኪናፋሶ ጋር 50 በመቶ፤ ከሴኔጋል ጋር 0 በመቶ፤ ከግብፅ ጋር 16.6 በመቶ እንዲሁም ከካሜሮን ጋር 16.67 በመቶ የማሸነፍ እድል ይኖረዋል፡፡