Administrator

Administrator

ዓለም ገና እንደተፈጠረችና ጊዜ መቆጠር ሲጀምር ማንከስ የተባለችው የቤት ድመት ጭራ ነበራት ይባላል። በጣም ግሩም

ጭራ። ረዥም፣ እንደ ነብር ዥንጉርጉር፣ የሚያኮራና የሚያጎማልል።
ማንከስ ድመት ኩሩ ናት። ጭራዋን ሽቅብ አቁማ ቀና ብላ ስትጎማለል ኩራቷ በማንም እንስሳ አይደረስበትም። ስታድንና

ስትተኛ በስተቀር ጭራዋን አትሸመልለውም።
የማንክስ ድመት ጠባይ ከመጠን ያለፈ ልበ-ሙሉነት፣ ከልክ-ያለፈ ራስን በራስ በማኖር ማመን፣ በፍፁም በሌሎች

አለመመራትና የራሷን ደመ-ነብስ መከተል ነበር።ታዲያ አንድ ጊዜ አደገኛ የጥፋት ውሃ ሊመጣ ሆነ። አምላክ በሰው ልጆች ድርጊት ተቆጥቶ ነው ይህ ጥፋት የሚደርሰው።
ስለዚህም ይማሩ ዘንድ ይሄ ጥፋት ውሃ መጣ።አምላክም ኖኅ መርከብ እንዲሰራና ከየእንስሳቱ ሁለት ሁለት እየያዘ በመርከቡ እንዲያመልጥ አዘዘው። ኖኅ መርከቡን ሠራ።
ለመሄድም ዝግጁ ሆነ። አምላክ ለሁሉም እንስሳት እንዲህ አለ፤ “ሁላችሁም ሁለት ሁለት እየሆናችሁ ወደ ኖኅ ሂዱ። ወደ መርከቡም ግቡ። እስከ ጎርፉ ፍፃሜ ቀን እሱ ይንከባከባችኋል” አላቸው።
ሁሉም እንደታዘዙት ፈጸሙ። አንዲት እንስሳ ብቻ ትዕዛዙን አልሰማ አለች። ይህች እንስሳ ማንከስ ድመት ናት።
“የምሰራው ስራ ስላለኝ ለመምጣት አልችልም። ገና አደን አለብኝ። ለምግቤ አይጥ ልፈልግ እሄዳለሁ” አለችና ወደ አደኗ
ተሰማራች። ሌሎቹ እንስሳት በመርከብ ተሳፈሩ።
ጥቂት ዝናብ ማካፋት ጀመረ። ኖኀ ያልገቡትን በማስገባት ሥራ ተጠመደ። ማንከስ ድመትንም “አይርፈድብሽ፣ በጊዜ ነይና
ተቀላቀይ። አሁኑኑ ነይ” አላት።
ማንከስም፤ “አሁን እንኳን ለመምጣት ዝግጁ አይደለሁም። ደግሞም አንተ በፈለግህበት ሰዓት ሳይሆን እኔ በፈለግሁበት ሰዓት
ነው የምሄደው” አለችና ጢሟን እያሸች፣ እየተጎማለለች ሄደች።ኖኅ የመጨረሻዎቹን እንስሳት ሲያስገባ ዝናቡ ዶፍ መጣል ስለ ጀመረ የመጨረሻ ጥሪ አደረገላት- ለማንከስ ድመት። በሩን
መዘጋጋት ቀጠለ። ልጆቹና  ቤተሰቦቹ መርከቡን እየጎተቱ ማንቀሳቀስ ጀመሩ።ማንከስ ድመት ጸጉሯን ዝናብ ሲያበሰብሰው ታወቃት። ቀዝቃዛና ዶፍ የቀላቀለ ዝናብ ነበር። ፍርሃትና ራዕድ አስከተለባት።
ይሄኔ ኖኅን አለመታዘዝ ጅልነት ነው ብላ አሰበች። ከሌሎቹ እንስሳት ጋር ወደ መርከቡ ካልሄደች የጎርፍ ሲሳይ እንደምትሆን ገባት።ዘላ ወደ መርከቡ ጥልቅ አለች። በሩ የመጨረሻውን ክፍተት እየዘጋ ነበር። ማንከስ ድመት ገብታ ከጨረሰች በኋላ ጭራዋ ታንቆ ቀረባት። በጣም አሳመማት። ስቃይ ሲበዛባት መጮህ ጀመረች። ኖኅ አዝኖ አከላትዋን አስለቀቀላት። ሆኖም ውቡን ጭራዋን
ሊያድንላት አልቻለም። እንደ ነብር ጅራት የተዥጎረጎረ ጭራዋ ተጎምዶ ወደቀ። በተጠራች ሰአት ያልመጣችው የማንከስ
ድመት ዘለአለሟን ጎራዳ ጭራ ሆና ቀረች።

***
ለማንኛውም ነገር ማርፈድ ጎጂ የመሆኑን ያህል፤ በምንፈለግ ሰዓት አለመምጣት እጅግ በጣም ጎጂ ነው። የጥፋት ውሃ

እስኪመጣ መጠበቅ ኋላ የእውር ድንብር መሄድን ያስከትላል። ወቅታዊ የሀገር ጥሪ ወቅታዊ ምላሽ ይፈልጋል።
የግለሰብ፣ የድርጅት ወይም የፖለቲካን ፍላጎት፣ ከሀገር ፍላጎት ማስቀደም የብዙሃንን ችግር ያወሳስባል። የብዙሃንን ብሶት

ያባብሳል። አልፎ ተርፎም ለውድቀት ይዳርጋል። የሕዝብን በደል ጩኸት፣ የህዝብን ወዮ ጥሪ አለመስማት የሀገርን ጉዳይ ቸል

ከማለት አንድ ነው። የገቡትን ቃል አለመፈጸም ለሀገር ጥሪ ጆሮ ዳባ ልበስ ከማለት አንድ ነው። በዲሞክራሲያዊነት ስም ኢ-

ዲሞክራሲያዊ መሆን የሀገርን አደራ ከመብላት አንድ ነው። ሲፋጅ በማንኪያ፣ ሲቀዘቅዝ በእጅ መብላት ከአታላይነት አንድ

ነው። ፍትሐዊነትን እንደ መመሪያ እየጠቀስን፣ አድልዎን በየፋይሉ ላይ ከፈረምን የጥፋት ውሃው አካል ነን ማለት ነው።

በመላው አገር ላይ የተንሰራፋውን ድህነት፣ ከአናት እስከ ግርጌ የወረረንን በሽታ፣ ከልሂቅ እስከ ደቂቅ የለከፈንን ሙስና፣ በበር

ስንሸኘው በመስኮት የሚገባውን ጦርነት፣ ልማት እያወራ ልፋት የሚያስከትለውን ዋልጌ ሃላፊ፤ ወዘተ የምናስወግድበትን

መንገድ በጋራ ለመቀየስ በልባዊ ዲሞክራሲያዊ ስሜት ካልተነሳሳን እንደ ድመቷ ጅራታችንን ተቆርጠን እንኳን የምንድንበት

የኖኀ መርከብ አይኖረንም።  ከየፖለቲካ ድርጅቱ  ከየቡድኑ ከየአይነቱ  ሁለት ሁለት ሰው ጭኖ ከጥፋት ውሃ የሚያድን

መርከብ እንኳ ከቶም የለንም። ሁሉም የጥፋት ውሃው ተሰምቶት ካልተረባረበ፣ በአንድ ኖኅ ቀርቶ በሺህ ኖሆች ሊሰራ የሚችል

መርከብ ከቶ አይኖረንም።
በእርዳታ ሊገኝ የሚችልን ገንዘብ ለማግኘት አለመቻል አንድ ጥፋት ነው። በእርዳታ የተገኘን ገንዘብ በአግባቡ አለመጠቀም

ከባድ ጥፋት ነው። በእርዳታ የተገኘን ገንዘብ በዚህም ሆነ በዚያ ምክንያት  ከነጭራሹ ሳይጠቀሙ መቅረት የጥፋት ውሃ ነው።

ህዝብ በበሽታ እያለቀ በህዝብ ስም የተገኘን ገንዘብ በቢሮክራሲያዊ ሰበብ ስራ ላይ አለማዋል አንድ ትውልድ ላይ ወንጀል

እንደመፈጸም የከፋ እኩይ ተግባር ነው።  
ለወቅታዊ ጥሪዎች ወቅታዊ ምላሽ ሊሰጡ የሚችሉ የፖለቲካ አውሎ ንፋስ በማነሳሳት “ጨሰ! አቧራው ጨሰ” የሚሉቱ

ሳይሆኑ፣ የሀገርና የህዝብ ችግር የሚቆረቁራቸው አስተዋይ ወገኖች ብቻ ናቸው። አስተዋይ ያልሆኑቱ በወቅታዊ ምላሽ ፈንታ

ወቅታዊ ምላስ ነው የሚሰጡት። ዛሬ ባለንበት ሁኔታ ለሀገሩ ቀና አሳቢውን ሃላፊነት የሚሰማውን፣ ለቅርብ ፍላጎት ሳይሆን

ለሩቅ እድገት የተነሳውን፣ ለጊዜያዊ ግምገማ ሳይሆን ለዘላቂ ግብ የቆመውን፣ ለድርጅት ስሜት የሚደሰኩረውን ሳይሆን ለሀገር

በመስጋት የሚቃጠለውን፣ አበጥሮ ለማየት አያዳግትም። “እንደምነህ አትበል ፊቱን እየው” ነውና።
አዲስ ሹም በመጣ ቁጥር ከዜሮ የመጀመር ፈሊጥ ሌላው የጥፋት ውሃ ማባባሻ ነው። በተጣለ መሰረት ላይ የቆመን ጠማማ

ማገር ማቃናት ወይም መንቀል አንድ ነገር ነው። መሰረቱን አልፈልገውም ብሎ እርጥብ-ከደረቅ ማንደድ ግን ሌላ ነገር ነው።  

ጎጂ ነው። “አይብ አይተው አሬራ ይደፋሉ” እንዲሉ አዲስ ሀሳብ ብልጭ ባለ ቁጥር በእጅ የያዙትን ሁሉ በትኖ ሆይ ሆይ ማለት

ብዙ መንገድ አያስኬድም። ስር የያዘን ነገር ማስተዋል ለማገርም ለጣራም አቅም ይሆናል። በአንጻሩ አዲስ ሹም አዲስ ስለሆነ

ብቻ ደግሞ ጭፍን ጥላቻ ማሳደር በጭራሽ አግባብነት የለውም። በአሮጌ አስተሳሰብ እንደ መኩራራት የሚያደነቁር

አመለካከት የለም። አዲስ ሹም፤ መዋቅርን፣ የሰው ሃይልን፣ አሮጌ አተያይን በአዲስ መልክ ለማሻሻል መጣሩ ነገን ለመቅረጽ

አንዱ ተስፋ ነው- ፍትሃዊ እስከሆነ ድረስ። ዲሞክራሲያዊ ባህል እስካለው ድረስ። ርቱእነትና ግልጽነት እስካልጎደለው

ድረስ። ለትክክለኛው ቦታ ትክክለኛ ሰው እሱ እስከሆነ ድረስ። “ጨካኝ እንጂ ሹም አትፍራ” የሚባለውም ይሄኔ ነው።
ሀገርን ከጎረቤት ሀገር፣ ሀገርን ከዓለም የሚያኖራት ዲሞክራሲያዊ ብስለትም ነው። ዲፕሎማሲያዊ አደራ የሀገር ጥሪ ነው።

ከመቼውም ጊዜ በላይ ዲፕሎማሲያዊ ብልህነት የሞትና ህይወትን መስመር የሚለይበት ወቅት ቢኖር ዛሬ ነው። የሀገር ጥሪን

መወጣት ከጥፋት ውሃ መዳን ነው። በጊዜ የኖኅ መርከብ መስራት ነው። በአጭር ጊዜ የኖኅ መርከብ መስራት ቢሳን ብዙ

ታንኳዎችን እየሰሩ መንገድን ማቀላጠፍ ነው። አቅም ግንባታ፣ ያለንን አቅም ከመጠቀም ነው የሚጀምረው። ሜዳው ላይ

መሮጥ ሳይቻል ተራራ መውጣት ዘበት ነውና። እንደ ጥንቱ፣ ሹሙ ሀገር ውስጥ ጥፋት ሲበዛበት የውጪ ዲፕሎማት አድርጎ

ገለል ማድረግ፣ ዛሬ ዘዴ ሳይሆን ሀገርን መበደል መሆኑ ፍንትው ብሎ የታየበት ዘመን ነው።
የተወሳሰቡት ችግሮቻችን አንዱ ካንዱ ጋር የተጠላለፉ መሆናቸው ብቻ ሳይሆን፣ እያንዳንዳቸው ስር የሰደዱ መሆናቸው ነው

አልነቀል እንዲሉ የሚያደርጋቸው።  በችጋር ላይ ችጋር እየተደራረበ ከድህነት በታች አድርጎናል። እጅግ ጥልቅ ድቀት

በመሆኑና የድህነታችን ቅርንጫፎች በመብዛታቸው ለድህነታችን ተጠያቂው እንኳ ማን እንደሆነ በውል ለመለየት ያቃተ

ይመስላል። ዛሬ ጫፉ ላይ የደረሰውን የኢኮኖሚ መቆርቆዝ የሰበቡን ምንጭ ካላየንና ካልፈታን የአናቱን ችግር አንቀርፈውም።

መፈክር እያሰገርንና በዘመቻ ሊፈቱ የሚችሉ ችግሮች ናቸው እያልን በምንረባረብባቸው ጉዳዮች ላይ ብዙ ሃብትና የሰው

ኃይል ከመፍሰሱ በፊት አስቦ፣ አበጥሮ የሚያይ አዋቂ ያሻቸዋል። ድህነት ስር መሰረት እንዳለው፣ የሚናገር ሳይታክት

የሚፈትሽ በአንድ አቅጣጫ እያየ ምርምር ጨርሻለሁ የማይል፣ ሆደ-ሰፊና አዕምሮ ብሩህ ሰው ያስፈልገናል። አሁንም አዲስ  

መንገድ ለመቀየስ የሚደፍር አዋቂ ሊኖር ይገባል።
አዋቂው “ሰበበኛ ድህነት ከማለዳ ይጀምራል” የሚለውን ተረት በቅጡ ለማጤንና ለማሳየት ዕውቀትም፣ ድፍረትም አያጣምና!

አርቲስት አብርሃም ወልዴ፣ ለሰርጉ ወጪ በሚል በጎፈንድሚ እና በተለያየ መንገድ ከሰበሰበው ከ2.2 ሚሊዮን ብር በላይ ገንዘብ ውስጥ 1.9 ሚሊዮን ብር በደቡብ ጉራጌ፣ በሰሜን ሸዋ ፍቼ ከተማ፣ በሰቆጣና በደብረብርሃን ለሚገኙ አራት የበጎ አድራጎት ተቋማት ለገሰ።
ገንዘቡ የተበረከተው ለጋበር የበጎ አድራጎት ድርጅት፣ ለፍቅር የተቀናጀ የማህበረሰብ ልማት ማህበር፣ በደብረብርሃን ለሚገኙ ተፈናቃዮችና በሰቆጣ 3 ወረዳዎች ለሚገኙ ከ30 ሺህ በላይ ተፈናቃዮች ነው፡፡
አርቲስት አብርሃም ወልዴና ባለቤቱ ወ/ሮ ማክዳ ኃ/ሚካኤል፤ ለጋበር በጎ አድራጎት 250 ሺ ብር፣ ለፍቅር የተቀናጀ የበጎ አድራጎት ማህበር 250 ሺ ብር፣ ለደብረብርሃን ተፈናቃዮች 400 ሺ ብር እንዲሁም በአበርገሌ በሳግብጂና በሰቆጣ ወረዳ ለሚገኙ ተፈናቃዮች 1 ሚሊዮን ብር፤ በድምሩ 1.9 ማሊዮን ብር ለግሰዋል፡፡
ሙሽሮቹ ከዚህ ቀደም ከዚሁ ለሰርግ ስጦታ ከወዳጅ ዘመድ ከተሰበሰበው ገንዘብ ላይ 300 ሺ ብር ለሜቄዶኒያ የአረጋዊያንና የአዕምሮ ህሙማን ማዕከል መለገሳቸው ይታወቃል።
አርቲስት አብርሃምና ባለቤቱ ማክዳ ለሰርጋቸው ከሰበሰቡት 2 ሚሊዮን 266 ሺህ 205 ብር ከ56 ሳንቲም ውስጥ በጎፈንድሚ የተሰበሰበው 31 ሺ 935 .20 ዶላር ሲሆን፤ ቀሪው ገንዘብ በብር የተሰበሰበ መሆኑ ታውቋል፡፡
ዛሬ ቀትር 7 ሰዓት ተኩል ላይ የገንዘብ ድጋፉን በደሳለኝ ሆቴል በተካሄደ ሥነስርዓት ላይ የተረከቡት የየተቋማቱ ተወካዮች፣ አርቲስት አብርሃምንና ባለቤቱን ወ/ሮ ማክዳን አመስግነው፣ ጥንዶቹ ትዳራቸው ፍሬያማ እንዲሆንላቸውም መልካም ምኞታቸውን ገልጸዋል፡፡
የቴሌግራም ቻናልችንን በመቀላቀል የአዲስ አድማስን መረጃ ይከታተሉ…

•  ሆስፒታሉ በ34 ሚ. ብር የተከፈለ ካፒታል የተመሰረተ ሲሆን፤ በአጠቃላይ 2.5 ቢ. ብር ይፈጃል


•  በመጀመሪያዎቹ  30  ቀናት አክሲዮን የሚገዙ ሁሉ፣ የመሥራች አባልነት መብት ያገኛሉ ተብሏል



በ17 የህክምና መሥራች አባላት የተመሰረተው ሐመር ተርሸሪ ሆስፒታል አ.ማ፣ ከመጪው ነሐሴ 1 ቀን ጀምሮ የአክስዮን ሽያጭ በይፋ እንደሚጀምር የተገለጸ ሲሆን፤ ከነሐሴ 1 እስከ 30፣ 2015 ዓ.ም ባሉት 30 ቀናት ውስጥ አክሲዮን የሚገዙ ሁሉ፣ የመሥራች አባልነት መብት ያገኛሉ ተብሏል፡፡

የሐመር ተርሸሪ ሆስፒታል አ.ማ መሥራች አባላት፣ በዛሬው ዕለት ረፋዱ ላይ በራስ አምባ ሆቴል፣ የአክሲዮን ሽያጩን አስመልክቶ ጋዜጣዊ መግለጫ ሰጥተዋል፡፡

ከሃሳቡ ጠንሳሽ አንዱ የሆኑትና የሆስፒታሉ ዋና ሥራ አስኪያጅ ዶ/ር ዳንኤል አዱኛ በመግለጫው ላይ እንደተናገሩት፤ሐመር ተርሸሪ ሆስፒታል አ.ማ፣ በ34 ሚሊዮን ብር የተመሠረተ ሲሆን፤ ሆስፒታሉን ገንብቶ ለማጠናቀቅ በአጠቃላይ 2.5 ቢሊዮን ብር እንደሚፈጅ ገልጸዋል፡፡

የሆስፒታሉ ሃሳብ መጀመሪያ ላይ የተጸነሰው በሥራ አስኪያጁ ዶ/ር ዳንኤልና በሙያ ባልደረባቸው እንደነበር የተጠቆመ ሲሆን፤ በኋላ ላይ ግን 17 ስመ ጥር የህክምናና የጤና ባለሙያዎች ሃሳቡን በመደገፋቸው ሐመር ተርሸሪ ሆስፒታል አ.ማ.ን በጋራ መመሥረታቸው ተመልክቷል፡፡

ከሳምንት በኋላ ነሐሴ 1 ቀን 2015 ዓ.ም የአክሲዮን ሽያጩ በይፋ እንደሚጀመር ያስታወቁት ሥራ አስኪያጁ፤ ከነሐሴ 1 ቀን ጀምሮ ባሉት 30 ቀናት ውስጥ አክሲዮኑን የሚገዙ ሁሉ፣ የመሥራች አባልነት መብት እንደሚያገኙ ይፋ አድርገዋል፡፡  

የአንድ አክስዮን ዋጋ 1ሺ ብር ሲሆን፤ አነስተኛው መግዛት የሚቻለው የአክሲዮን መጠን 50 (50ሺ ብር) እንደሆነና ከፍተኛው  መግዛት የሚቻለው የአክሲዮን መጠን ደግሞ 100ሺ (100 ሚሊዮን ብር) መሆኑ ተነግሯል፡፡

በመግለጫው ላይ ስለ ሆስፒታሉ ምሥረታ ማብራሪያ የሰጡትና ከመሥራች አመራር አባላት አንዱ የሆኑት ዶ/ር መሰለ ተሆነ፣ የሆስፒታሉ ራዕይ፣ በ2030 ኢትዮጵያውያን ለህክምና ወደ ውጭ ለመሄድ ያለባቸው እንግልት ተቀርፎ ማየት መሆኑን ጠቁመዋል፡፡ ሆስፒታሉ በዓይነቱም ሆነ በአገልግሎት ጥራቱ ከአገራችንም አልፎ በምሥራቅ አፍሪካ ቀዳሚ ሆኖ ማየትም ራዕያቸው እንደሆነ አመልክተዋል፡፡  

በወጣትና አንጋፋ የህክምናና የጤና ባለሙያዎች ጥምረት የተመሰረተው ሐመር ተርሸሪ ሆስፒታል አ.ማ፤ በኢትዮጵያ የመጀመሪያው ተርሸሪ ሆስፒታል መሆኑን ያወሱት ዶ/ር መሰለ፤ ሰፋ ያሉ የህክምና አገልግሎቶችን እንደሚሰጥና ትምህርትና ምርምርን ያካተተ የልህቀት ማዕከል እንደሚኖረው ተናግረዋል፡፡

የሆስፒታሉን ዓላማዎች ሲያብራሩም፤ በውጭ አገራት ይሰጡ የነበሩ ህክምናዎችን በአገር ውስጥ መስጠትና በኢትዮጵያ የህክምና ቱሪዝምን ማነቃቃትና ማስፋፋትን በዋነኝነት የጠቀሱ ሲሆን፤ በዚህም ለህክምና የሚወጣ የውጭ ምንዛሪን በመቀነስ፣ይልቁንም ለአገሪቱ የውጭ ምንዛሪን ማስገኘት የሚቻልበት ዕድል እንዳለ አንስተዋል፤ዶ/ር መሰለ፡፡     

ይህንን ለኢትዮጵያ ህዝብ ትልቅ ፋይዳ ያለውን ተርሸሪ ሆስፒታል እውን ለማድረግ በአገር  ውስጥም ሆነ በውጭ ያሉ ኢትዮጵያውያን ፣ አክሲዮን በመግዛት፣ እንዲሁም በዕውቀታቸው፣ በጊዜያቸውና በሃሳባቸው አስተዋጽኦ በማድረግ ታሪክ እንዲሰሩም፣ የመሥራች ቦርድ አመራሮቹ  ጥሪ አቅርበዋል፡፡  

ከመሥራቾቹ አንዷ የሆኑትና የማህጸን ስፔሻሊስት መሆናቸውን የገለጹት ዶ/ር መቅደላዊት መስፍን፣ የሆስፒታሉን ምሥረታ በተመለከተ በሰጡት አስተያየት፤ “ሆስፒታሉ ለዚህ በመድረሱ ደስተኞች ነን፤እኛም የአቅማችንን ማበርከት መቻላችን ትልቅ ነገር ነው፤ ወደፊት ደግሞ በሙያችን የሚፈለግብንን  አገልግሎት በመስጠት የላቀ አስተዋጽኦ እናበረክታለን ብዬ አምናለሁ፡፡” ብለዋል፡፡

ሌላው የመሥራች አባል ዶ/ር ኃይለማርያም ታዲዮስ በበኩላቸው፣ ሐመር ተርሸሪ ሆስፒታል በመመሥረቱ የተሰማቸውን ደስታ ገልጸው፣ በአገር ውስጥም ሆነ በውጭ የሚገኙ ኢትዮጵያውያን አብረዋቸው እንዲሰሩ መልዕክት አስተላልፈዋል፡፡

 - ውሳኔው ያልተጠበቀና ድንገተኛ ነው ተብሏል


        የአማራ ክልል ፕሬዚዳንት ዶ/ር ይልቃል ከፋለ፤ የፀጥታ ጉዳዮች አማካሪያቸውን ከሃላፊነት ማንሳታቸውን ምንጮች ጠቆሙ። ከጸጥታ ጉዳዮች አማካሪው በተጨማሪ የክልሉ የሰላምና ጸጥታ ቢሮ ምክትል ሃላፊም ከሃላፊነታቸው ተነስተዋል።
በያዝነው ሳምንት መጀመሪያ በክልሉ ፕሬዚዳንት ዶ/ር ይልቃል ከፋለ ፊርማ በወጣው የስንብት ደብዳቤ፣ ከሃላፊነታቸው የተነሱት የክልሉ የሰላምና ጸጥታ ቢሮ በምክትል ሃላፊነት ደረጃ የርዕሰ መስተዳድሩ የጸጥታ ጉዳዮች አማካሪ አቶ ከፋለ እሱባለውና የቢሮው ምክትል ሃላፊ ኮማንደር መንገሻ አውራሪስ ናቸው።
ሁለቱ የስራ ሃላፊዎች ከሃላፊነታቸው እንዲነሱ ከመደረጋቸው አንድ ቀን ቀደም ብሎ በተደረገ የስራ ግምገማ “ጥሩ አፈጻጸም አሳይተዋል” በሚል የተመሰገኑ መሆኑን የጠቆሙት ምንጮች፤ አሁን ከሃላፊነታቸው ተነስታችኋል የመባላቸው ጉዳይ ድንገተኛና ያልተጠበቀ እንደሆነ አመልክተዋል።
የርዕሰ መስተዳድሩ የጸጥታ ጉዳዮች አማካሪ የነበሩት አቶ ከፋለ እሱባለው፣ በዚህ ሃላፊነት ረዘም ላሉ ጊዜያት መቆየታቸውን ያመለከቱት ምንጮች፤ ቀደም ሲል ክልሉን ሲያስተዳድሩ ለነበሩ አምስት ርዕሰ መስተዳድሮች የጸጥታ ጉዳዮች አማካሪ ሆነው ማገልገላቸውን አስታውሰዋል፡፡
በርዕሰ መስተዳደሩ በተፈረመ ደብዳቤ ከሃላፊነታቸው የተነሱት ሁለቱም የስራ ሃላፊዎች የደረሳቸው የስንብት ደብዳቤ፤ “የተሰጥዎትን ተግባርና ኃላፊነት በአግባቡ ያልተወጡ በመሆኑ ከሃላፊነት የተነሱ መሆኑን አሳውቃለሁ”። የሚል እንደሆነም ታውቋል።



የኒጀር ወታደሮች በብሔራዊው ቴሌቪዥን መፈንቅለ መንግሥት!!


        በምዕራብ አፍሪካዊቷ ሀገር ኒጀር ወታደሮች በብሔራዊው ቴሌቪዥን መፈንቅለ መንግሥት አወጁ። ሕገ-መንግሥቱን መበተናቸውን፤ ሁሉም የመንግሥት ተቋማት ለጊዜው ሥራ ማቆማቸውንና የሃገሪቱ ድንበሮች መዘጋታቸውን ይፋ አድርገዋል።
ከረቡዕ ጀምሮ የኒጀር ፕሬዝደንት ሞሐመድ ባዙም በወታደሮች ቁጥጥር ሥር እንዳሉ ተዘግቧል።
የአሜሪካ ውጭ ጉዳይ ሚኒስትር አንቶኒ ብሊንከን፤ ዩናይትድ ስቴትስ ለፕሬዚዳንቱ “ድጋፍ እንደምታደርግ” ቃል እንደገቡም ተደምጧል።
የተባበሩት መንግሥታት ዋና ፀሐፊ አንቶኒዮ ጉቴሬዝ፤ ፕሬዚዳንቱን እንዳገኟቸው ገልጸው ድርጅታቸው ድጋፍ እንደሚያደርግላቸው ተናግረዋል።
ፕሬዚዳንት ባዙም፣ በምዕራብ አፍሪካ እስላማዊ ተዋጊዎችን ለመዋጋት በሚደረገው ጥረት የምዕራባዊያን አጋር ናቸው።
የኒጀር ጎረቤት የሆኑት ማሊና ቡርኪና ፋሶ በቅርብ ዓመታት በተመሳሳይ በመፈንቅለ መንግሥት ምክንያት ታምሰው እንደነበር አይዘነጋም። በሁለቱም ሃገራት ወደ ሥልጣን የመጡት ወታደራዊ አስተዳደሮች የቀድሞ ቅኝ ገዥ ከሆነችው ፈረንሳይ ጋር ያላቸውን ግንኙነት አቋርጠዋል።
ልክ እንደ ማሊና ቡርኪና ፋሶ ሁሉ ማሊም በፈረንሳይ ቅኝ ተገዝታ ነበር።
ረቡዕ ዕለት ዘጠኝ የወታደር መለዮ በለበሱ ሰዎች ተከበው በቴሌቪዥን መስኮት መግለጫ የሰጡት ኮሎኔል ሜጀር አማዱ አብድራማኔ፤ “እኛ የመከላከያና የፀጥታ ኃይሎች የምታውቁትን መንግሥት ከሥልጣን አውርደናል” ብለዋል።
የሃገሪቱ ሁሉም ተቋማት ለጊዜው ሥራ እንደሚያቆሙ የገለጹት ኮሎኔሉ፤ ሚኒስትሮች የቀን ተቀን ሥራውን እንደሚመሩ አስታውቀዋል፡፡
 “ሁሉም የውጭ አገራት ጣልቃ እንዳይገቡ እንጠይቃለን። ሁኔታዎች እስኪረጋጉ በምድርም ሆነ በአየር ድንበራችንን ዘግተናል” ብለዋል።
አክለውም፤ ላልተወሰነ ጊዜ ከምሽት 4 ሰዓት እስከ ንጋት 11 የሚቆይ ሰዓት እላፊ መታወጁን  አሳውቀዋል።
ወታደሮቹ በቴሌቪዥን ቀርበው ይህን ካሉ በኋላ፤ ብሊንከን ፕሬዚዳንት ባዙም እንዲለቀቁ ጥሪ አቅርበዋል። ኒው ዚላንድ ሳሉ ለጋዜጠኞች መግለጫ የሰጡት ሚኒስትሩ፤ “ይህ በግላጭ ሥልጣንን በኃይል ለመያዝና ሕገ-መንግሥቱን ለመናድ የሚደረግ ጥረት ነው” ብለዋል።
የምዕራብ አፍሪካ የምጣኔ-ሃብት ጥምረት የሆነው ኤኮዋስ በኒጀር የተካሄደውን መፈንቅለ መንግሥት ያወገዘ ሲሆን፤ የኤኮዋስ ተዋካይ የሆኑት የቤኒኑ ፕሬዚዳንት ፓትሪስ ታሎን ለሽምግልና ወደ ዋና ከተማዋ ኒያሜይ አቅንተዋል።
ረቡዕ ዕለት በዋና ከተማዋ በርካታ ቁጥር ያላቸው ሰልፈኞች ለፕሬዚዳንት ባዙም ያላቸውን ድጋፍ ለመግለጽ አደባባይ ወጥተዋል። የቢቢሲ ዘጋቢ እንደተመለከተው ደግሞ የፕሬዚዳንቱ ታማኝ የሆኑ ወታደሮች ብሔራዊውን ቴሌቪዥን ታጥቀው ሲጠብቁ ነበር።
ምንም እንኳ መፈንቅለ መንግሥት ያሰቡ ወታደሮች ሰልፈኞችን ለመበተን ተኩስ ቢከፍቱም፣ ከተማዋ ከሞላ ጎደል ሰላማዊ ነበረች።
ኒጀር ከማሊና ከናይጄሪያ በሚነሱ እስላማዊ ጂሃዲስቶች ከ2015 ጀምሮ ተወጥራ ቆይታለች። ከአል-ቃይዳና ከኢስላሚክስ ስቴት ጋር ግንኙነት ያላቸው ታጣቂዎች ኒጀር ውስጥ ሠፍረዋል።
የፈረንሳይና የሌሎች ምዕራባዊያን መንግሥት አጋር የሆኑት ፕሬዚዳንት ባዙም በምርጫ ወደ ሥልጣን የመጡት በ2021 ነው።
(ቢቢሲ)




                           ጥበበኛው ሽማግሌ ስለ ስኬት


       በጥበበኛነቱ ወደሚታወቅ አንድ ሽማግሌ ዘንድ አንድ ወጣት መጣና፤ “በህይወቴ ስኬታማ መሆን እፈልጋለሁኝና ምን ማድረግ እንዳለብኝ ንገረኝ” አለው፡፡ ጥበበኛው ሽማግሌም የወጣቱን ዓይኖች ትኩር ብሎ ሲመለከታቸው ስኬትን ለማግኘት ያለውን ቁርጠኛነትን ተረዳና እንዲህ ሲል ጠየቀው፤ “በህይወትህ በጣም የምትወደው ምግብ ምንድነው?” ወጣቱም ምንም ሳያመነታ፤ “እናቴ ጋግራ የምታበላኝን ዳቦ ነው አብልጬ የምወደው” በማለት መለሰ፡፡
ጥበበኛው ሽማግሌ አሁንም የወጣቱን አይኖች ትኩር ብሎ እየተመለከታቸው፤ “እሺ አሳ ለማጥመድ ፈልገህ ወደ ሀይቅ ዳር ብትሄድ አሳውን ለማጥመድ ማጥመጃው ጫፍ ላይ ምን አይነት ምግብ ታደርጋለህ?” ሲል ጠየቀ፡፡ ወጣቱም ፈጣን በሆነ ምላሽ፤ “ትላትሎችን አደርጋለሁኝ!” በማለት መለሰ፡፡ በዚህ ጊዜ ጥበበኛው ሽማግሌ ለወጣቱ ልጅ፤ “ለምን? አንተ የምትወደው ምግብ እናትህ የጋገረችውን ጣፋጭ ዳቦ ነው፡፡ ለምንድነው አንተ የምትወደውን ዳቦ ትተህ ለአሳው ትላትል የምትወስድለት?” በማለት መስቀለኛ ጥያቄን አቀረበለት፡፡ ልጁም ትንሽ አሰብ አደረገና፤ “አሳውን ለማጥመድ ስሄድ ማሰብ ያለብኝ እኔ ስለምወደውና ስለምፈልገው ምግብ ሳይሆን አሳው ስለሚወደውና ስለሚፈልገው ምግብ ነው!” በማለት ተናገረ፡፡ በዚህን ጊዜ ጥበበኛው ሽማግሌ ፈገግ ብሎ ወደ ወጣቱ ልጅ እየተመለከተ፤ “በል እንግዲህ ልጄ! ስኬትን የማግኛው ምስጢርም አሁን አንተ የተናገርከው ነገር ነው፡፡ እኛ የምንፈልገውና የምንወደው ነገር እንዳለ ሁሉ ስኬትም የሚፈልገውና የሚወደው ነገር አለ፡፡ ስለዚህ ስኬትን ማግኘት የምትፈልግ ከሆነ አንተ የምትወደውንና የምትፈልገውን ነገር ከማድረግ ይልቅ ስኬት የሚፈልገውን  ነገር ተግብር!” በማለት ምክሩን ለግሶት ጉዞውን ቀጠለ፡፡
በህይወታችን ማሳካት የምንፈልጋቸውን ነገሮች ከግብ ለማድረስ የምንሻ ከሆነ፡ ነፍስያችን የምትፈልገውንና የምትወደውን ነገር ገታ በማድረግ ማግኘት የምንፈልገው ስኬት የሚፈልገውንና የሚወደውን ተግባር መፈጸም  አለብን፡፡ ይህ ነው የአጭሩ ታሪክ ትልቅ መልዕክት!
ያማረ ስኬት ለሁላችን!
(መፅሐፈ ሬድዋን)



     ከአጼ ኃይለሥላሴ ዘመን አንስቶ በአራት መንግሥታት ውስጥ ያለፉትና ከመጻህፍት አዟሪነት እስከ ከፍተኛ የጦር አዛዥነት የደረሱት ኮሎኔል ፈቃደ ገብረየስ የጻፉት “የኔ መንገድ“ የተሰኘ ግለ-ታሪክ (ኦቶባዮግራፊ)፣ ባለፈው ቅዳሜ ሐምሌ 15 ቀን 2015 ዓ.ም  ከሰዓት በኋላ በጊዮን ሆቴል ግሮቭ ጋርደን ተመርቋል፡፡
በ653 ገጾች በ8 ክፍሎችና በ68 ምዕራፎች የተቀነበበው መጽሐፉ፤ የኮሎኔሉ የቀድሞ አለቆችና የደርግ ዘመን ከፍተኛ የጦር አዛዦች፣ ቤተሰቦችና ወዳጆች እንዲሁም የሚዲያ ባለሙያዎች በታደሙበት ሥነስርዓት ነው የተመረቀው፡፡
የመጽሐፍ አዟሪነት ዘመናቸውን በምረቃው ሥነሥርዓት ላይ ያወሱት ኮሎኔል ፈቃደ ገብረየስ፤ “እኔ መጽሐፍ ስነግድ እነ ሻምበል አፈወርቅ ዮሐንስን፣ አቤ ጉበኛን፣ ክቡር ደራሲ ሚካኤል ከበደን በአካል አውቃቸው ነበር፡፡” ሲሉ ተናግረዋል፡፡
ከአጼ ኃይለሥላሴ ጋር ድንገት መንገድ ላይ ተገናኝተውም መጽሐፍ እንደሸጡላቸው ደራሲው በምርቃት ሥነስርዓቱ ላይ አስታውሰዋል፡፡ በመጽሐፋቸው ውስጥም ገጠመኙን ከትበውታል፡፡
“የኔ መንገድ“ የተሰኘውን የኮሎኔል ፈቃደ ገብረየስ ግለታሪክ መጽሐፍ፣ የአርትኦት ሥራ ያከናወኑት ታዋቂው ጋዜጠኛና ደራሲ ዘነበ ወላና  የሥነጽሁፍ ባለሙያው ባዩልኝ አያሌው ሲሆኑ፤ ሁለቱም ስለመጽሐፉ አጫጭር ሙያዊ አስተያየታቸውን ሰጥተዋል - በምርቃት ሥነስርዓቱ ላይ፡፡
የኮሎኔል ፈቃደ የቀድሞ አለቃ የነበሩትና የደርግ ዘመን ከፍተኛ የጦር አዛዥ ብርጋዴር ጀነራል ካሣዬ ጨመዳና ሌሎችም በመድረኩ ላይ ስለ ባለታሪኩ የሚያውቁትን ምስክርነት ሰጥተዋል፡፡
ኮሎኔል ፈቃደ ከዚህ ቀደም አራት ያህል መጻሕፍት ለንባብ አብቅተዋል፡፡ ”የአመራር ሳይንስ እና ጥበብ”፣ ”ድርጅታዊ የጤና ምርመራ”፣ ”ስትራቴጂ - ሥራ አመራር” እና ”የዓለም ሀገሮች” ይሰኛሉ፡፡ አምስተኛውንና ባለፈው ቅዳሜ የተመረቀውን  “የኔ መንገድ“ የተሰኘ ግለታሪክ ለምንና እንዴት እንደጻፉት በመጽሐፉ መግቢያው ላይ እንዲህ ያስረዳሉ፡-
“አንዳንድ ወዳጆቼ “ለምን የህይወት ታሪክህን አትጽፍም?“ ሲሉኝ፣ “እኔ ምን ታሪክ አለኝ?“ እያልኩ ነገሩን ጉዳዬም ሳልለው ቆየሁ፡፡ አንድ ቀን ጠዋት አንደኛው ልጄ ብስራት ፈቃደ በጨዋታ መሃል ድንገት “ጋሼ የህይወት ታሪክህን ግን ለምን አትጽፍም? በሕይወት እያሉ እኮ ታሪካቸውን የሚጽፉ ጥቂቶችና የታደሉ ናቸው። ሌሎቹ እኮ ልጆቻቸው ናቸው የሚጽፉላቸው“ አለኝ፡፡ እኔም “ምን ታሪክ አለኝና እጽፋለሁ? ልጻፍ ብልስ አስር ገጽስ መጻፍ እችላለሁ እንዴ?“ ብዬ መለስኩለት፡፡ “ግለ ታሪክህን ስትጽፍ እኮ ያንተን ታሪክ ብቻ አይደለም የምትጽፈው፡፡ በተለያዩ አጋጣሚዎች ያገኘሃቸውን ሰዎችንና ድርጊቶች እንዲሁም ገጠመኞች ጭምር እንጂ።  አንተ ደግሞ በተለያዩ ጊዜያት ስታጫውተን ልብ እንዳልኩት ብዙ ህይወት አሳልፈሃል፡፡ በዚህ ሂደትም ከብዙ ሰዎች ጋር ተገናኝተሃል፡፡ የሚገራርሙ ገጠመኞችም አሉህ፡፡ ብዙ ሰውም የሚጽፈው  እኮ ይህንኑ ነው፡፡ ለማሳተም እንኳን ብትቸገር አዘጋጅቶ ማስቀመጡ አንድ ነገር ነው።“ ብሎ የምመልሰውን ለመስማት በአንክሮ ተመለከተኝ፡፡ የምመልሰው ባጣ “እስቲ ላስብበት“ ብዬው ጨዋታችንን ቋጨን፡፡--” በዚህ መንገድ ነው ቅዳሜ  ለምርቃት የበቃው መጽሐፍ የተወለደው፡፡
የራሳቸውን ታሪክና ከህይወታቸው ጋር የተገናኙ የሌሎች ሰዎችን ታሪኮች እንዲሁም ገጠመኞች ያካተቱበትን ይህን መጽሐፍ ለምን “የኔ መንገድ“ እንዳሉት ሲገልጹም፤  “--ሁሉም ሰው የራሱ የተለየ ታሪክ አለው። እያንዳንዱ ሰው የተጓዘበት የህይወት ልምዱ የአንዱ ከሌላው ፈጽሞ የተለየ ነው፡፡ ልክ እንደ እጃችን አሻራ ያንዱ ከሌላው ጋር በምንም አይመሳሰልም፡፡ አሁን ላይ የዕድሜዬ ቆጣሪው 69ኛው ዓመት ላይ ያሳያል፡፡ በዚህ ረጅም ዓመታት እኔ የተጓዝኩበትና የመጣሁበት መንገድ፣ የኖርኩበትና ያለፍኩበትም የህይወት ልምድ እንዲሁ ከሌላው የተለየ ነው፡፡ ለዚህም ነው የመጽሐፌን ርዕስ ”የኔ መንገድ” በማለት የሰየምኩት፡፡--” ብለዋል፡፡
ከመጽሐፉ አርታኢዎች አንዱ የሆነውና የቀድሞው የአዲስ አድማስ የረዥም ጊዜ ጸሐፊ ባዩልኝ አያሌው በምረቃው ሥነስርዓት ላይ በሰጠው ሙያዊ አስተያየት፣ የምዕራፎቹ ስያሜዎች ጠሪ ናቸው ብሏል፡፡ ማራኪ ናቸው ለማለት ይመስላል፡፡ ጥቂቶቹን ለማሳያ ያህል፡- “ከኢህአፓ ጋር መርካቶ ተዋወቅን“፣ “ባድመ ግንባር ላይ ያገኘሁት ጎረቤቴ“፣ “አይ ጨበራ ጩርጩራ ፓርክ“፣ “የሞስኮ ጎረምሶች አንቆራጠጡን“፣ “የባዳ ዘመዳችን - መወለድ ቋንቋ ነው“፣ “አባባ ጃንሆይን መንገድ ላይ አገኘኋቸው”፣ “የተነፋው ጎማ ተነፈሰ” ወዘተ ይገኙባቸዋል፡፡ አርታኢው እውነት ብሏል፤ጠሪ ናቸው፡፡
አርታኢ ባዩልኝ አያሌው በመጽሐፉ ላይ የሚታዩ ጥንካሬዎች ብሎ በቀዳሚነት የጠቀሰው፣ በበርካታ መረጃዎች የበለጸገ መሆኑን ነው፡፡ ለዚህም በምክንያትነት ያቀረበው፤ ደራሲው በሦስት መንግሥታት ያገለገሉ መሆናቸውን፣ በውትድርናና በሲቪል ሙያዎች ንቁ ተሳታፊ የነበሩ መሆናቸውንና የአስገራሚ ገጠመኞች ባለቤት ለመሆን መታደላቸውን ነው፡፡
ግለታሪኩ የቀረበበት ወይም የተተረከበት ቋንቋ ዕጹብ ድንቅ መሆኑንም ያወሳል- የሥነጽሁፍ ባለሙያው ባዩልኝ አያሌው፡፡ “--የኮሎኔሉ ዘመነኞችም ሆኑ የአሁኑ ወጣት ትውልድ እኩል ሊረዱትና ሊያጣጥሙት በሚችል ቋንቋ ነው የቀረበው፡፡ --ከዛም አልፎ አንዳንድ ጊዜ ጸሃፊው ከመደበኛው የቃላት አጠቃቀም ሆን ብሎ በማፈንገጥ የአራዳ ብለን የምንጠራውን ዘዬም ሲገለገሉ እናስተውላለን፡፡ ይህም ያልበዛ በመሆኑና በዛችው አውድ ውስጥ የተወሰነ በመሆኑ የሚረብሽ የሚባል ዓይነት አይደለም፡፡” ሲል አስተያየቱን ይሰጣል፡፡
ኮሎኔል ፈቃደ ገብረየስ አብዛኞቹን ምዕራፎች ወይም ርዕሶች የሚከፍቱት በታዋቂ ጸሃፍትና ገጣምያን አባባሎችና ግጥሞች ነው፤ ይህም የመጽሐፉን ታሪክ ተነባቢና ማራኪ ከማድረጉም ባሻገር ለማስተላለፍ ያሰቡትን ሃሳብ ወይም መልዕክት ጠንካራ አድርጎላቸዋል። ጸሃፊው ለርዕሰ ጉዳያቸው የሚሆኑ ተስማሚ አባባሎችና ግጥሞችን ለማግኘትና ለመምረጥ ብዙ መጻሕፍትና ሰነዶችን በማገላበጥ መልፋታቸውንም መገንዘብ ይቻላል፡፡ ይህም ትጉህ ደራሲ መሆናቸውን ያስመሰክራል፡፡
ለምሳሌ ”ኮሎኔል ካሣ ገ/ማርያም” ከሚለው ርዕስ በታች ከደራሲ ብርሃኑ ዘሪሁን ”የበደል ፍጻሜ” መጽሐፍ የወሰዱትን አባባል አስፍረዋል፡፡ “ደፋሮች አንዴ ብቻ ይሞታሉ፤ በፍርሃት ያለማቋረጥ ሲሞቱ የሚኖሩ ደግሞ ብዙ ናቸው።” (ብርሃኑ ዘሪሁን- የበደል ፍፃሜ ገፅ 311)
"ክፍል 4 ከባህር ማዶ መልስ” የሚለው ምዕራፍ ደግሞ በድምጻዊ መሀሙድ አህመድ የግጥም ስንኞች ነው የተከፈተው፡፡ ”አንዴ በመከራው አንዴ በደስታዬ/ ስንቱን ያሳየኛል ይኼ ትዝታዬ” (ድምፃዊ መሀሙድ አህመድ) ይላል፡፡
”ወታደራዊ ሊቁ - ጄነራል ጻድቃን ገብረትንሳኤ” የሚለውን ርዕሳቸውን እንዲሁ  በገጣሚ ነቢይ መኮንን የግጥም ስንኞች ከፍተውታል፡፡
“… ሰው እያለ አጠገባችን፣
ቅንነቱን ማየት ሲያቅተን፣
ከኛው አብሮ በሕይወት ቆሞ፣
መልካ ስሙን መጥራት ሲያንቀን፣
ሰው ካልሞተ ወይ ካልሄደ አይነሳም እንላለን።
እንዲህ እያልን
ስንቱን ጠቢብ እየሸኘን፣
አበባውን ቀጥፈን፣ አበባ እናስቀምጣለን!!”
“የኔ መንገድ“ ግለታሪክ መጽሐፍ፤ ለአገር ውስጥ በ600 ብር፣ ለውጭ አገራት በ25 ዶላር ለሽያጭ ቀርቧል፡፡ ዘገባዬን ደራሲው በመጽሐፉ መግቢያ ላይ በተጠቀሙበት የሲ.ሲ. ኮልተን አባባል ልቋጭ፡፡
እንዲህ ይላል፡- “ደራሲ መሆን ሦስት ችግሮች አሉት፡፡ ለህትመት የሚመጥን ጽሁፍ መጻፍ፤ የሚያሳትሙ ቅን ሰዎች መፈለግ፤ የሚያነቡትን አስተዋይ ሰዎች ማግኘት፡፡”

    ቡዳፔስት ለምታስተናግደው 19ኛው የዓለም አትሌቲክስ ሻምፒዮና 21 ቀናት ቀርተዋል። በዚህ የዓለም ሻምፒዮና ላይ ኢትዮጵያ
   ቡድን ከሚጠበቅባቸው ውድድሮች ዋነኛው ማራቶን ነው። ስፖርት አድማስ የማራቶን ቡድኑን ዝግጅት አስመልክቶ ይህን ልዩ ዘገባ አዘጋጅቷል።


        “ወርቅን አካቶ አራት ሜዳልያዎችን እናገኛለን ብዬ እገምታለሁ፡፡” አሠልጣኝ ሃጂ አዴሎ
የኢትዮጵያ ማራቶን ቡድን ዋና አሰልጣኝ ሃጂ አዴሎ ለዓለም ሻምፒዮናዎች የተደረገው ዝግጅት አርኪ ነው። ይህን አስመልክቶ ለስፖርት አድማስ አስተያየት ሲሰጥ “የማራቶን ቡድኑ መሰባሰብ የጀመረው ከ2 ወራት በፊት። ላለፉት 6 ሳምንታት ልምምድ እየሰራን እንገኛለን። በየአቅጣጫው ነው የምንሰራው፤ የተወሠነ ቦታ የለንም። አንዳንዴ እንጦጦ እንሔዳለን፤ ሱልልታ እንወጣለን አቃቂ፣ ሰበታ፣ ሰንዳፋ እያልን በአራቱም አቅጣጫ እየወጣን እየሰራን ነው፡፡” ብለዋል። በ18ኛው ዓለም አትሌቲክስ ሻምፒዮና ላይ የኢትዮጰያ ቡድን በታምራት ቶላና በጎይተቶም ገብረስላሴ በሁለቱም ፆታዎች የወርቅ ሜዳልያዎች መውሰዱና በሁለቱም ፆታዎች  የሻምፒዮናው ሪከርዶች መመዝገቡ ይታወቃል። ከሁለቱ የወርቅ ሜዳልያዎች  ባሻገር ሞሰነት ገረመውም የብር ሜዳልያ ተጎናፅፏል፡፡ በአጠቃላይ ባለፈው ሻምፒዮና በማራቶን 3 ሜዳልያዎች ነው የተገኙት፡፡ ቡዳፔስት ላይስ ምን ይጠበቃል? አሰልጣኝ ሃጂ በምላሻቸው ‹‹ዘንድሮ ልጆቹ በጣም ጥሩ ላይ ነው ያሉት፡፡ ጥሩ ልምምድም እያደረጉ ነው፡፡ አንዳንድ ጊዜ ኢትዮጵያውያኖች የምንቸገረው በአየሩ ሁኔታ ነው፡፡ የቡዳፔስት አየር ሞቅ ሳይል አይቀርም፡፡ ምናልባት ይህ ሁኔታ ትንሽ ይረብሸናል ብለን ከማሰብ ውጭ አገሪቱ አሏት የተባሉ አትሌቶች ነው የተሰባሰቡት፡፡ ጥሩ ነገር እናመጣለን ብለን ነው የምናስበው፡፡ በሻምፒዮኖቻችን ተጨማሪ አንድ አትሌት ማሰለፋችን ቀላል አይደለም፡፡ሌሎች ሶስት ሲያሰልፉ እኛ አራት መያዛችን ቡድኑን ያጠናክራል። እውነት ለመናገር ከኢትዮጵያ ጋር ትልቁ ተፎካካሪ የምንለው ኬንያዎችን ናቸው፡፡ የኛም አትሌቶች አመቱን ሙሉ ጥሩ ውጤት ሲያስመዘግቡ ቆይተዋል። ሁሉም ተገናኝተው በተለያዩ ውድድሮች አብረው ሮጠዋል። ፉክክሩ ብዙ የሚያሳስብና የሚያስፈራ አይደለም፡፡ ዘንድሮ ለዓለም ሻምፒዮናው የተያዙ አትሌቶች በጣም ጠንካሮች ናቸው፡፡ ስለዚህም ወርቅን አካቶ አራት ሜዳልያዎችን እናገኛለን ብዬ እገምታለሁ፡፡ ቢያንስ አራት፣ ግን አምስትም ሊሆን ይችላል” ብሏል።
“እኛ በሁለቱም ፆታዎች ስድስቱም ሜዳሊያዎች ቢመጡልን ደስተኞች ነን፡፡” አሠልጣኝ ገመዳ ደደፎ
ከዓለም ሻምፒዮናው የማራቶን ቡድን አሰልጣኞች ሌላኛው ገመዳ ደደፎ ይባላል፡፡ በአትሌቲክስ ስልጠና ውስጥ ከ15 ዓመታት በላይ ልምድ ያለው ሲሆን በአሰልጣኝነትና በረዳት ማናጀርነት እየተሳካለት ነው፡፡ በተለይ ባለፉት ሶስት ዓመታት በግማሽ ማራቶንና በማራቶን ስኬታማ የሆኑ  በርካታ አትሌቶችን  እያሰራ ይገኛል። ለዓለም ሻምፒዮናው ስለተዋቀረው የኢትዮጵያ ቡድን ሲናገር ‹‹አትሌቶቹ በዓለም ደረጃ ካሉት የተሻሉ ናቸው፡፡ አሁን ከሚገኙ ምርጥ አትሌቶች ጋርም ተፎካካሪዎች እንደሆኑ አምናለሁ፡፡ በያዙት የልምምድ ትጋት ከቀጠሉ እና፤ ምናልባት የአየር ንብረቱ የማይፈትን ከሆነ የተሻለ ውጤት እንደሚያመጡ አስባለሁ፡፡ ባለፈው ሻምፒዮና ኦሬጎን ላይ አየሩ በጣም የተመቸ ነበር፡፡ ሞቃታማ አልነበረም፡፡ ይህም ለተሻለ ውጤት አግዟቸዋል፡፡ ዘንድሮ በቡድን ውስጥ ሁለት የወቅቱ ሻምፒዮኖች መያዛችን ከሌሎች የተሻለ እድል ይፈጥርልናል፡፡ በአትሌቶቹ መካከል ከአምናው የተሻለ መቀናጀትና መረዳዳት ካለ ከወዲሁ ጥሩ ውጤት እንደሚገኝ ግምት የሚያሳድር ነው፡፡›› ነው ብሏል።
ለኢትዮጵያ ቡድን  በዓለም ሻምፒዮናው የማራቶን ትንቅንቅ ዋናው ተፎካካሪዎች የኬንያ አትሌቶች ናቸው፡፡ አሰልጣኝ ገመዳ በዚህ ጉዳይ ላይ ሲያስረዳ ‹‹እንግዲህ ሜዳ የገባ ሁሉ ለመወዳደር ነው። በዓለም ሻምፒዮናው ላይ የሚሳተፉት አብዛኛዎቹ አትሌቶች ለምሳሌ በሴቶች ከ2 ሰዓት ከ22 ደቂቃ በታች የገቡ ናቸው፡፡ በሞቃታማ አየር ንብረት ላይ የተሻለ ብቃት ያላቸው አትሌቶችም ይኖራሉ፡፡ የኛ ልጆች ደጋ ላይ የተወለዱ ናቸው። የአየር ሁኔታው በተለይ ሂሚውዲቲው ከፍ ያለ ከሆነ በውድድሩ ላይ ተፅእኖ ያሳድራል፡፡ በተለይ አፍሪካውያን ሊከብድ የሚችል ነው፡፡ በአጠቃላይ ግን ቱታ ያወለቀ ሁሉ ተወዳዳሪ ነው፡፡ እኛ በሁለቱም ፆታዎች ስድስቱም ሜዳሊያዎች ቢመጡልን ደስተኞች ነን፡፡ ማንም ለመሸነፍ፤ ማንም ለመቀደም አይሄድም፡፡ ሁሉም እዛ የሄደው የተሻለ ውጤት ለማምጣት ነው፡፡ በተቻለን መጠን የራሳችንን ጥረት እናደርጋለን፡፡ በመጨረሻም ያገኘነውን በደስታ ተቀብለን እንመለሳለን፡፡  ለዓለም ሻምፒዮናው በተያዘው ቡድን ካለፈው ሻምፒዮና በተሻለ በሴቶች ጠንከር ያለ ስብስብ ነው ያለው ሲነጻጸር ውጤት እንጠብቃለን፡፡›› የሚል ምላሽ ሰጥቷል።
“አትሌቶቹም ሆነ ማናጀሮቻቸው ካምፖችን እንዲገነቡ ማበረታታት ያስፈልጋል፡፡” አሰልጣኝ ሻምበል ቶሎሳ ቆቱ
ሻምበል ቶሎሳ ቆቱ ከኢትዮጵያ ቡድን ጋር ከ9 በላይ የዓለም ሻምፒዮናዎችን ተካፍለዋል። በባህሬን የአትሌቲክስ ቡድን ዋና አሰልጣኝነትም ከፍተኛ ልምድ ያካበቱ ናቸው፡፡ በአሁኑ ወቅት በኢትዮጵያ አትሌቲከስ ፌደሬሽን የብሔራዊ ቡድን አሰልጣኞችን በሚያስተባብሩበት ሃላፊነት እየሰሩ ናቸው፡፡ ‹‹የዓለም ሻምፒዮና ማለት የአገር ውድድር ከዚያም አህጉር ውድድር በማለፍ የሚደረግ ነው  መላው ዓለም እንደኦሎምፒክ ትልቅ ትኩረት ሰጥቶ የሚሳተፍበት ነው፡፡ መላው ዓለም ምርጥ አትሌቶችን ይዞ የሚሳተፍበት ነው፡፡ የዓለም ሻምፒዮን መባል ለማንኛውም አትሌት ታላቅ ክብር መሆኑም ይታወቃል፡፡›› በማለት የዓለም ሻምፒዮናን ታላቅነት ሻምበል ቶሎሳ ይገልጻሉ።
ከቡዳፔስት በፊት በዓለም ሻምፒዮና ኢትዮጵያ ላስመዘገበችው ወርቃማ ገድል በርካታ ታላላቅ አትሌቶች ተደጋጋሚ ውጤት በማስመዝገብ ታሪክ ሰርተዋል፡፡ ለዚህ ምስጥሩ ምንደነው የሚል ጥያቄም ከስፖርት አድማስ ቀርቦላቸውም ‹‹ምስጥሩ ስራ ነው፡፡ ስራን በስርዓት መስራት፡፡ ማንኛውም አትሌት ስራውን ከአሰልጣኙ ጋር ሆኖ በስነምግባር ማከናወን አለበት፡፡ በፊት በአብዛኛው በተፈጥሮ ነው፡፡ ዛሬ ላይ ብዙ የስልጠና ዘዴዎችና የቴክኖሎጂ ድጋፎች ይኖራሉ፡፡ በሳይንሳዊ ግኝቶች አትሌቶች ራሳቸውን አዋህደው በሚሰሩበት ዘመን ላይ ደርሰናል፡፡ በፊት በነበሩ አትሌቶች የቡድን ስራው ጥሩ ነው፡፡ አሁን በያዝናቸው አትሌቶችም ይህ መንፈስ እንዲኖር ነው እየሰራን የምንገኘው። ወደ ፌደሬሽኑ ስመጣ ይህንኑ ለማዳበር ነው፡፡ አትሌቶች ለአገራቸው ቢያንስ በውድድር ላይ ተረዳድተው እንዲሰሩ ነው፡፡ የማራቶን ቡድኑን እንደምትመለከተው ከአሰልጣኞቹ ጋር በአንድ ላይ እየሰሩ ነው፡፡ በሌሎች የውድድር ርቀቶችም ይህንን ተግባራዊ እያደረግን ነው።”
የዓለም ሻምፒዮናው ዝግጅት በስፖርት መሰረተ ልቶች አለመሟላት የተጋፈጠባቸውን ሁኔታዎች በተመለከተ ሲናገሩ “ድሮ በአዲስ አበባ የነበረው የልምምድ ስፍራ አንድ ነበር አሸዋ ሜዳ፡፡ ከዚያም አዲስ አበባ ስታድዬም ነው፡፡ ዛሬ አትሌቱም በዝቷል ቦታውም እየጠበበ ነው፡፡ ስለዚህ እኛ ከልምዳችን የምንረዳው እንደሌሎች አገሮች ከከተማ ወጣ ብሎ የሚገኝ የልምምድ ካምፕ የለንም፡፡ የልምምድ ካምፕ ቢኖረን አትሌቶች አይቸገሩም ነበር፡፡ ለወደፊቱ ፌደሬሽኑም ሆነ መንግስት መገንባት ያለበት የልምምድ ካምፕ ነው፡፡ ከከተማ ወጣ ብሎ በሚገኝ ስፍራ ላይ ቢሰራ በጣም ጥሩ ነው፡፡ ለምሳሌ ኬንያን ብትወስድ የተለያየ ቦታ ላይ በተለያየ አልቲትዩድ የልምምድና የስልጠና ካምፖች ተገንብተዋል። አትሌቶቻቸው ከተማ ሳይገቡ በልምምድ ካምፖቻቸው ተዘጋጅተው በዚያው ነው ወደውጭ አገር የሚሄዱት፡፡ ስለዚህም እኛም ያን የሚመስል መሰረተልማት ለወደፊቱ መሰራት ይገባናል። በመንግስት ደረጃ እንደዚህ አይነት የስፖርት ልማቶች እንዲገነቡ ቅድሚያ ትኩረት መስጠት ያስፈልጋል፡፡ አስቀድሞ የነበሩ አትሌቶች ውጤታማ ከሆኑና ከፍተኛ ጥቅም ሲያገኙ ተመሳሳይ የስፖርት ልማቶችን እንዲገነቡ አልገፋፋናቸውም፡፡ ኬንያ ውስጥ አትሌቶች ብቻ ሳይሆኑ ማናጀሮቻቸውም የስልጠና የልምምድ ካምፖችን በተለያዩ ስፍራዎች ገንብተዋል፡፡ አትሌቶቹም ሆነ ማንጀሮቻቸው ካምፖችን እንዲገነቡ ማበረታታት ያስፈልጋል።” በሚል ሃሳባቸውን ሰጥተዋል። ሻምበል ቶሎሳ ቆቱ ለስፖርት አድማስ እንደገለጹት ፌደሬሽኑን የሚመሩት ፕሬዝዳንቷም፤ ተቀዳሚ ፕሬዝዳንቱም በአትሌቲክስ ውስጥ ያለፉ መሆናቸው እንደ አትሌትም እንደአመራርም ጥሩ ለመስራት እያገዛቸው ነው፡፡ ኢትዮጵያ በቡዳፔስት ላይ ለሚኖራት ተሳትፎ ይህ የአንድነት መንፈስ እጅግ አስፈላጊ ነው። “ቡዳፔስት ላይ ከተቻለ ያለፈውን ውጤት ማስከበር ነው የምጠብቀው፡፡ አቅማችን ከተሻለ ካለፈው የበለጠ ውጤት ማስመዝገብ ይቻላል፡፡ በወንዶች ሺ እና ሺ ሜትር የያዝናቸው አትሌቶች በወቅታዊ ብቃታቸው ጥሩ ደረጃ ላይ ናቸው፡፡ የእነሱ ውጤት ከተሻሻለና በማራቶን ያለፈው ውጤት ከተደገመ ከኦሬጎን የተሻለ ውጤት እናመጣለን ብዬ እገመታለሁ፡፡” ብለዋል ሻምበል ቶሎሳ።
“ለአትሌቶች የልምምድ መስሪያ የሚሆን 10 ኪ.ሜትር ያህል የስፖርት መሰረተ ልማት ጎን ለጎን በአስፓልትም በኮረኮንችም  ቢዘጋጅ…” የዓለም ሻምፒዮኑ  ታምራት ቶላ
አትሌት ታምራት ቶላ በዓለም ሻምፒዮናው ጥሩ ልምድ ያለው አትሌት ነው። በ2017 ለንደን ላይ የብር ሜዳሊያ ካገኘ በኋላ በ2022 ደግሞ የወርቅ ሜዳልያውን ከሻምፒዮናው ሪከርድ ጋር ወስዷል። “ቡዳፔስት ለሚደረገው ሻምፒዮና ሶስት ሳምንት ገደማ ነው የቀረን፡፡ ጥሩ ዝግጅት ላይ ነን። አንድ ቡድን ሆነን ዝግጅቱን በስነስርዓት እየሰራን ነው፡፡ ከአምናው የተሻለ ውጤት ለማስመዝገብ በልምምድም ያለንን ሂደት አጠናክረነዋል፡፡ በግልም በቡድንም ለኢትዮጵያ ጥሩ ነገር እናመጣለን ብዬ እገምታለሁ፡፡” በማለት የቡዳፔስቱን ዝግጅት ገልጾታል። ኦሬጎን ላይ ከተመዘገበው ምን እንማራለን በሚል ከስፖርት አድማስ ተጠይቆ “ባለፈው ሻምፒዮና ለተመዘገበው ውጤት ዋናው ነገር የቡድን መንፈስ ነው፡፡ ዘንድሮ ከአምና በተሻለ በፌደሬሽኑ በኩል አንድ ላይ ተሰብስበን ስንሰራ ነው የቆየነው፡፡ አምና በመስማማት አንድ ላይ ሰርተን ጥሩ ውጤት አምጥተናል፡፡ ዘንድሮ ያንን በማሻሻል ነው እየሰራን የምንገኘው፡፡ አንድ ላይ ስንሆን ጥሩ ውጤት ይመጣል፡፡ አሰልጣኞቻችን የሚሰጡትን ምክር በአግባቡ ስራ ላይ ማዋል ይገባል፡፡” የሚል ምላሽ ሰጥቷል።
ከልምምድ መስራርያ ቦታዎች ጋር በተገናኘ ያለው ችግር ግን በጣም የሚያሳስብ ነው፡፡ በወጣቶች ስፖርት አካዳሚ በሳምንቱ አጋማሽ ላይ በተገኘንበት ወቅት ከዓለም ሻምፒዮናው ቡድን የማራቶን ስብስቡ ነበር ትራኩን እየተጠቀመ የነበረው፡፡ ይህ የአካዳሚው ትራክ በዓለም ሻምፒዮናው ዝግጅት ስራ የበዛበት ይመስላል፡፡ ፌዴሬሽኑ የዓለም ሻምፒዮናው ቡድን ያሉትን የልምምድ ስፍራዎች በፈረቃ ለመጠቀም ብዙ ሰርቷል። ከአትሌቶችና ከአሰልጣኞች ጋር በመመካከር ነው የተሰራው። ከዚያም ባሻገር በክፍያ የሚሰራባቸውን የልምምድ ስፍራዎችን ለመጠቀም ተሞክሯል። በአትሌቲክስ ከፍተኛ ውጤት ያላት አገር በስፖርት መሰረተ ልማት በተለይ ለአትሌቲክስ ብዙ መስራት እንደሚያስፈልግ የሚያመለክት ነው፡፡ በማራቶን የዓለም ሻምፒዮናነቱን ለማስጠበቅ ወደ ቡዳፔስት የሚጓዘው ታምራት ቶላ በዚሁ ጉዳይ ላይ አስተያየት ሲሰጥ ‹‹እኛ አገር በልምምድ ስፍራዎች ዙርያ በጣም ብዙ ያልተመቻቹ ነገሮች አሉ፡፡ በትራክም፤በአስፋልትም፤ በኮረኮንችም የምንሰራባቸው ብዙዎቹ ቦታዎች ተበላሽተዋል፡፡ ማራቶን ሯጮች በመሆናችን ብዙ ልምምድ የምንሰራው አስፋልት ላይ ነው። በሄድንበት ሁሉ አስፋልቱ የተፈቀደው ለመኪና ብቻ ነው የሚመስለው፡፡ ከመኪኖች ጋር እየተጋፋን ነው የምንሰራው፡፡ ብዙውን ጊዜ ልምምድ ላይ የሚያደናቅፉ ሁኔታዎች ይገጥሙናል፡፡ አደጋም ይደርሳል፡፡ እየሮጥን በሚበር መኪና እና በክላስ ጩሀት መሳቀቅ አለ፡፡ በድካም ውስጥ ሆነን የሚበር መኪና እያሰቀቀን ነው የምንሰራው፡፡ በፈጣሪ ሐይል ነው እሰከዛሬ ያለነው፡፡ በሰበታ እና ሰንደፋ ነው አትሌቶች ለስራ የሚወጡት፡፡ ብዙ የሚያስቸግሩ ሁኔታዎች አሉ፡፡ እኔ ለአገራችን የማስበው ቢያንስ በመንግስት ደረጃም ቢሆን በሚመለከተው አካል፤ ለአትሌቶች የልምምድ መስሪያ የሚሆን 10 ኪሎ ሜትር ያህል  የስፖርት መሰረተ ልማት ጎን ለጎን በአስፓልትም በኮረኮንችም  ቢዘጋጅ ነው፡፡ በአውሮፓና በአሜሪካ ለህዝብ ብቻ ክፍት የሚሆኑ ተመሳሳይ ቦታዎች ተከልልው መዘጋጀታቸውን አይቻለሁ፡፡ ብስክሌት እንኳን የማይገባበት ወጣቶችና ስፖርትኞች የሚሰሩበት ልማት አለ፡፡ በአደጉ አገራት ብዙ ከተሞች ላይ እንደዚህ አይነት መሰረተ ልማቶች ተገንብተዋል፡፡ እኛም አገር ላይ  በሚገባን  ደረጃ ይህ አይነቱ የስፖርት መሰረተ ልማትን በአዲስ አበባ ዙርያና በሌሎች ከተሞችም መገንባት ያስፈልጋል፡፡ በዓለም አደባባይ በዓለም ሻምፒዮናም ሆነ በኦሎምፒክ ኢትዮጵያ የምትጠራው በአትሌቲክስ ነው፡፡ ስለዚህም ቢያንስ ይህን ታሳቢ አድርጎ መፍትሄ ሊደረግ ይገባል፡፡ እኛ ያሉትን ፈተናዎች እየተጋፈጥን ብናልፍ ለሚመጣው ትውልድ ግን መፍትሄው መሰራት አለበት፡፡ አሁን በትራክ መሰረተልማቶች አለመሟላት በሁሉም የሩጫ ውድድሮች ላይ እንዳንሳተፍ ነው ያደረገን። በአጭርና መካከለኛ ርቀት ያለን ተሳትፎ እየደከመ ነው የመጣው፡፡ አሁን ያለን አንድ ትራክ ብቻ ነው ይህን ለሁሉም የርቀት መደቦች ለመገልገል በቂ ሊሆን አይችልም፡፡ ይህን አስቦ የአዲስ አበባ ስታድዬም ትራክም ሌሎችም ትራኮች ተሟልተው በመገንባት ለአትሌቶች ዝግጁ ቢሆኑ ጥሩ ነው፡፡ ምክንያቱም ይህም እንደ ሃገር ልማት ሊታይ ይገባል። ሃገርን የሚያስተዋውቅ ይሆናል፡፡” በማለት ምክሩን ለግሷል።
የኢትዮጵያ ማራቶን ቡድን በቡዳፔስት
በቡዳፔስት የዓለም ሻምፒዮና የኢትዮጵያ ማራቶን ቡድን እጩ አትሌቶች የተለዩት ከ2 ወራት በፊት ነው። በአትሌቲክስ ፌዴሬሽኑ ዋና አሰልጣኞች ሆነው የተመረጡት ሐጂ አዴሎና ገመዳ ደደፎ ናቸው። በማራቶን ቡድኑ ያለፈው ሻምፒዮኖች ታምራት ቶላና ጎይተቶም ገ/ስላሴ በቀጥታ የተሳትፎ ትኬታቸውን ቆርጠዋል። በእጩነት የተያዙት ደግሞ በሁለቱ ጾታዎች 10 አትሌቶች ናቸው። በወንዶች ፀጋዬ ጌታቸው (በታላቅ ማራቶን የነሐስ ሜዳልያ ያገኘ፤ በዓለም የማራቶን ደረጃ  7ኛና በ2022  የአምስተርዳምና የሪያድ ማራቶኖችን ያሸነፈ)፤ ጫላ ዴሶ (በዓለም  የማራቶን ደረጃ 13ኛ፣ የቶኪዮና የፓሪስ ማራቶኖች አሸናፊ)፤ ልዑል ገ/ስላሴ (የዓለም የማራቶን ደረጃ 16ኛ፣ በሮተርዳምና በለንደን  ማራቶኖች 2ኛ ደረጃ ያገኘ)፤ ሰይፉ ቱራ (በዓለም የማራቶን ደረጃ 12ኛ በ2021 የቺካጎ ማራቶን ያሸነፈ) እንዲሁም መሀመድ ኢሳ (በቶኪዮ ማራቶን 2ኛ በመውጣት ልምድ ያለው) ናቸው። በሴቶች ደግሞ ወርቅነሽ ኢዴሳ (በዓለም የማራቶን ደረጃ 17ኛ፣ የፕራግ ማራቶንን ያሸነፈች፣ በበርሊንና በቶኪዮ ማራቶኖች 4ኛ ደረጃ ያገኘች)፤ መገርቱ አለሙ (በዓለም የማራቶን ደረጃ 6ኛ፣ የቫሌንሽያ ማራቶን ያሸነፈች)፤ ፀሃይ ገመቹ (የዓለም የጎዳና ላይ ሩጫ ደረጃ 5ኛ በአምስተርዳምና፤ በቶኪዮ ማራቶኖች 2ኛና 3ኛ ደረጃ ያገኘች)፤ እንዲሁም ያለምዘርፍ የኋላው (በዓለም  የጎዳና ላይ ሩጫ 1ኛ ደረጃ፣ በ2022 የለንደንና የሀምበርግ ማራጾንን ያሸነፈች) ናቸው።
ከላይ በሁለቱም ጾታዎች ከተዘረዘሩት 5 እጩ አትሌቶች መካከል በስልጠና ቆይታቸው፣ ወቅታዊ ብቃታቸውና ጤንነታቸው የተሻሉት አትሌቶች ነሐሴ 20 እና 21 ላይ የዓለም ሻምፒዮናውን እንደሚሮጡ ይጠበቃል።
ከቡዳፔስት በፊት
ከቡዳፔስት በፊት ኢትዮጵያ ባለፉት 18 የዓለም ሻምፒዮናዎች በማራቶን የወሰደቻቸው ሜዳልያዎች ብዛት 15 ደርሰዋል፡፡  በወንዶች 3 የወርቅ፤ 6 የብርና 3 የነሐስ ሜዳልያዎች ናቸው፡፡ በሴቶች ደግሞ 2 የወርቅና የነሐስ ሜዳሊያዎች ተነኝተዋል።
በወንዶች ሶስቱን የወርቅ ሜዳልያዎች  ታምራት ቶላ በ2022፣ ገዛኸኝ አበራ በ2001 እንዲሁም ሌሊሳ ዴሲሳ በ2019 አግኝተዋል፡፡ 6 የብር ሜዳልያዎችን የወሰዱት ከበደ ባልቻ በ1983፤ ሌሊሳ ዴሲሳ በ2013፤ የማነ ፀጋየ በ2015፤ ታምራት ቶላ በ2017 እንዲሁም ሞስነት ገረመው በ2019ና በ2022 እኤአ ነው፡፡ 3 የነሐስ ሜዳልያዎችን ደግሞ ፀጋዬ ከበደ በ2009፤ ፈይሳ ሌለሳ በ2011 እንዲሁም ታደሰ ቶላ በ2013 እኤአ ላይ አግኝተዋል፡፡ በሴቶች ደግሞ ሁለቱ የወርቅ ሜዳሊያዎች በማሬ ዲባባ በ2015 እንዲሁም ጎይተቶም ገ/ስላሴ በ2022 ያገኟቸው ሲሆን አሰለፈች መርጊያ በ2015 1 የነሐስ ሜዳሊያ ወስዳለች።


   በደቡብ አሜሪካዊቷ ሀገር ብራዚል አስገራሚ የፍቅር ታሪክ ተሰምቷል።
ኢማኑኤላ የተባለችው እንስት ስልኳን ሞጭልፏት ካመለጠው ግለሰብ፣ ፍቅር ይዞኛል ማለቷን ኒውዮርክ ፖስት አስነብቧል።
ስሙ ያልተጠቀሰው ግለሰብም ስልኳን ከሰረቀ በኋላ የተሰማውን ስሜት አጋርቷል።  “በስልኳ ላይ የተነሳቻቸውን ምስሎች ስመለከት ልዩ ስሜት ተሰማኝ፤ ምን አይነት ውበት ነው ስል ተደነቅኩ፤ ለምን ሰረቅኳት ስልም ተጸጸትኩ” ሲልም ያስታውሳል።
የስልክ ስርቆት ያጣመራቸውን ጥንዶች በጋራ ቃለመጠይቅ ያደረገላቸው ጋዜጠኛም ጥያቄውን ያስከትላል፤ “ስልኳን ብቻ ሳይሆን ልቧንም ነዋ የሰረቅከው?” የሚል ጥያቄ፤ እሱም ጊዜ ሳይወስድ “በትክክል!” የሚል ምላሽ ሰጥቷል።
ጥንዶቹ በስልክ የጀመሩት ንግግር ወደ ፍቅር ግንኙነት አድጎ ባለፉት ሁለት አመታት ደጋግመው ተገናኝተዋል።
የጥንዶቹ ቤተሰቦች ስለ ጉዳዩ መስማታቸው ባይታወቅም፣ በትዊተር መንደር ግን መነጋገሪያ ዜና ሆኗል።
አንድ አስተያየት ሰጪ፤ “ፍቅር የማይለውጠው ነገር የለም፤ የኢማኑኤላ ፍቅር ግለሰቡን ከስርቆት እንደሚገላግለው  እተማመናለሁ” የሚል ሃሳቡን አጋርቷል።
ሌላኛው ደግም፤ “ጉዳዩ ቀልድ ቢመስልም ዜናው የተሰማው ከብራዚል ነውና ሊሆን  የሚችልበት እድል ሰፊ ነው” ብሏል።
ባልተጠበቀ ሁኔታ የፍቅር ግንኙነት የሚጀምሩ ሰዎች ቁጥር ቀላል አይደለም። የብራዚሉ ክስተትም ያልተለመደ ይምሰል እንጂ በተለያዩ ሀገራት መሰል ዜናዎች ተደምጠዋል ብሏል፤ ኒውዮርክ ፖስት በዘገባው።
(አል- ዓይን)



ህጻናት በትችት ካደጉ፣ ውግዘትን ይማራሉ፡፡
ህጻናት በጥላቻ ካደጉ፣ ጠበኝነትን ይማራሉ፡፡
ህጻናት በፍርሃት ካደጉ፣ ጭንቀትን ይማራሉ፡፡
ህጻናት እየተሾፈባቸው ካደጉ፣ ዓይናፋርነትን
ይማራሉ፡፡
ህጻናት በመመቅኘት ካደጉ፣ ቅናትን ይማራሉ፡፡
ህጻናት በመቻቻል ካደጉ፣ ትዕግስትን ይማራሉ፡፡
ህጻናት እየተበረታቱ ካደጉ፣ ልበሙሉነትን
ይማራሉ፡፡
ህጻናት እየተካፈሉ ካደጉ፣ ቸርነትንና ለጋስነትን
ይማራሉ፡፡
ህጻናት በሙገሳና በምስጋና ካደጉ፣ ማድነቅን
ይማራሉ፡፡
ህጻናት በታማኝነትና በቅንነት ካደጉ፣ እውነትንና
ፍትህን ይማራሉ፡፡
የእርስዎስ ልጆች እንዴት እያደጉ ነው??
(-ዶሮቲ ኤል. ኖልቴ-)

Page 9 of 665