Administrator

Administrator

በዶ/ር ኤርሲዶ ሌንደቦ የተዘጋጀውና፣ “ኑሮMap” የተሰኘው የለውጥ መፅሐፍ ውስጥ ከሰፈረ ታሪክ አንዱን ነቅሰን እንድንመለከት ወደድን፡፡ ከዓመታት በፊት የአገራችንን ችግር የተነበየና መፍትሔውንም ያሳየ ግሩም መጽሐፍ ነው፡፡ ከዚህ ቀደም የጠቀስነው ቢሆንም፣ ለዛሬም ይሰራልና ደግመነዋል፡፡
የኮንስትራክሽን ኩባንያውን ከጊዜ ወደ ጊዜ እያሳደገ የመጣ ወጣት መሃንዲስ፤ ኩባንያውን ይበልጥ የሚያሳድጉ ሶስት ፕሮጀክቶችን በኮንትራት ተረክቦ ግንባታ ጀምሯል፡፡ ነገር ግን ሁሉም ነገር አልጋ በአልጋ አይደለም፡፡ የስኬት መንገድ ላይ የተለያዩ ችግሮች ያጋጥማሉ፡፡ መፍትሔ በማበጀትና የስኬት ጥረትን በመቀጠል ነው ስኬቶችን እውን ማድረግ የሚቻለው፡፡
ወጣቱ መሀንዲስ የስራ ማስኬጃ ገንዘብ ቢያጥረውም፤ ከባንክ ብድር ለማግኘት ጊዜ የሚፈጅ ስለሆነበት፤ በግል ከሚያውቀው ሰው፤ በተወሰነ ጊዜ ከወለድ ጋር የሚመለስ ገንዘብ ተበድሯል፡፡ ችግሩ፤ በተስማሙበት የጊዜ ቀጠሮ እዳውን ለመመለስ አልቻለም። አበዳሪው እንዳያገኘው መሸሽና ስልኩን መዝጋት፤ እንደ መፍትሔ ሆኖ ታይቶታል፡፡
መፍትሔው ግን ሌሎች መዘዞችን ጐትቶ አምጥቷል፡፡ አንደኛ፤ ሌሎች ደንበኞቹና ተባባሪዎቹም በስልክ ሊያገኙት ስላልቻሉ፤ የተለያዩ ጥቅሞችን እያጣ ነው፤ እየተጐዳ ነው፡፡ ሁለተኛ፤ ከአበዳሪው ስለሸሸ ብቻ ችግሩን ያስወገደ ይመስል፤ እዳውን ለመክፈል የሚያስችል ዘዴ ማፈላለግ አቁሟል፡፡ ሶስተኛ፤ መፍትሔው ከአንድ ሳምንት በላይ አልዘለቀም፡፡ መቼም፤ ከሰው ተደብቆ የኮንስትራክሽን ፕሮጀክቶችን መምራት አይችልም፡፡
አበዳሪው፤ በሰው በሰው አጠያይቆ፤ የግንባታ ቦታው ድረስ መጥቶ አፋጠጠው፡፡ አሁንስ መፍትሔው ምንድነው? ምናልባት፤ በድርድር ለማግባባት ጥረት ቢያደርግና፤ ወለዱን በማሻሻል የክፍያ ጊዜውን ለማራዘም ቢስማሙስ? ያኔ ወጣቱ መሃንዲስ ፕሮጀክቶቹን አጠናቅቆ፤ በቀላሉ እዳውን መክፈል ይችላል - የተወሰነ ያህል ተጨማሪ ጥረትና ገንዘብ ቢያስፈልገውም፡፡ ወጣቱ መሃንዲስ፤ ይህንን መፍትሔ አልመረጠም፡፡
አበዳሪውን በፈገግታ ተቀብሎ፤ ከከተማ ውጭ ስልክ የማይሰራበት ቦታ ሄዶ እንደነበር በውሸት ለማሳመን ከሞከረ በኋላ፤ ቼክ ፈርሞ ሰጠው፡፡ በቃ በዚሁ ተገላገለ፡፡
ግን እስከ መቼ? ባንክ ውስጥ የነበረውን ገንዘብ ለስራ አውጥቶ እንደጨረሰው ያውቃል:: ቢሆንም ለጊዜው፤ ከአበዳሪው ተገላግሏል፤ ችግሩን ፈታ፡፡ ምን ዋጋ አለው? መፍትሔው አልሰራም፡፡ አበዳሪው ቼኩን ለመመንዘር ወደ ባንክ ከሄደ በኋላ ባዶ እጁን ወደ ወጣቱ መሃንዲስ ተመለሰ፤ እዳውን ለማስከፈል፡፡ ብቻውን አይደለም፡፡ ፖሊስም ጭምር እንጂ፡፡
ወጣቱ መሐንዲስ፤በደረቅ ቼክ አጭበርብረሃል ተብሎ ተከሰሰ፡፡ ከተፈረደበት ብዙ ነገር ያጣል፤ እዳውን ከካሳ ጭምር ይከፍላል፤ ለጠበቃና ለቅጣት ተጨማሪ ገንዘብ ያወጣል፤ የገንዘብ እጥረቱን ይበልጥ የሚያባብስ፡፡ በዚያ ላይ ፍ/ቤት በመመላለስና በእስር፤ የስራ ጊዜውን ያባክናል፤ ፕሮጀክቶቹ ይዳከማሉ - የገንዘብ ምንጮቹን ይጐዳል፡፡ “የማያዛልቅ ጥገና” እንዲህ ነው፡፡
ዋናው መሰረታዊው ችግር፤ የገንዘብ እጥረት ቢሆንም፤ ወጣቱ ግን ሁነኛ መፍትሔ እንደመፈለግ፤ በቁንጽል የችግሩ ውጫዊ ምልክት ላይ አተኮረ - የአበዳሪ ጭቅጭቅ ላይ፡፡ ለአሁኗ ቅጽበት፤ ወይም ለዛሬ ብቻ፤ ከአበዳሪ ጭቅጭቅ ለመገላገል ጊዜያዊ መፍትሔዎችን (የማያዛልቁ ጥገናዎችን) መርጧል፡፡ ውሳኔውንና ድርጊቱን ከነገ ህይወቱ ጋር አያይዞ ለማየት አልሞከረም፡፡ የገንዘብ እጥረት ችግሩን ከማባባስ አልፎ፤ የገንዘብ ምንጩን የሚጐዳ ተጨማሪ ችግር እንደሚመጡበት ለማሰብ አልፈለገም፡፡
የማያዛልቅ ጥገና፤ የተለመደ የሰዎች ባህርይ ነው፡፡ ብዙዎቻችን፤ የዋና ዋና ነገሮችን መስተጋብር በማገናዘብ፤ መሰረታዊውን ችግር ከመጋፈጥ ይልቅ፤ የችግሩ ውጫዊ ምልክት ላይ ብቻ እናተኩራለን፡፡
ውጫዊው የችግር ምልክት፤ ለብቻው በቁንጽል ጐልቶ ስለሚያስጨንቀን፤ በአሁኗ ቅጽበት ለብቻው ገንኖ ስለሚያዋክበን፤ ፈጣን የህመም ማስታገሻና የችግር ማብረጃ ለማግኘት እንጣደፋለን - ሌሎች ዋና ዋና ነገሮችንና ነገን ሳናስብ፡፡
ጊዜያዊ ማብረጃ፤ የችግሩ ምልክት እንዲጠፋ ያደርግልናል፡፡ ግን፤ ዋናው ችግር ስላልተወገደ፤ ምልክቱም ከጊዜ በኋላ መልኩን ቀይሮ ወይም ከቀድሞው ገዝፎና በርክቶ እንደገና መከሰቱ አይቀርም፡፡ በጊዜያዊ ማስታገሻ ራሳችንን በማታለል፤ ለመሰረታዊው ችግር ሁነኛ መፍትሔ ስላላበጀንለት፤ የችግሩ ምልክት ተባብሶ ሲመጣብንስ?
ድሮ የለመድነውን ጊዜያዊ ማስታገሻ (ችግር መሸፈኛ) መጠኑን ከፍ አድርገን፤ ሌላም ማስታገሻ ጨምረን እንሞክራለን፡፡ ይህም ተመልሶ ችግሩን እያባባሰ፤ አዙሪቱ እየከረረ ይሄዳል፡፡ አንዳንድ ሰዎች ሱስ እስኪመስልባቸው ድረስ ይቀጥላሉ፡፡
ካነበብነው የአሳዎች ታሪክ እንዳየነው፤ ለምግብ የሚሆን የባህር ዕፅዋት የተከሉት አሳዎች፤ የምግብ እጥረትን ለዘለቄታው ለማስወገድ ሳይሆን ለቅጽበት ረሃባቸውን ለማስታገስ ነበር የጓጉት። ዕፅዋቱ ደግሞ፤ ለማደግ ጊዜ ያስፈልጋቸዋል፡፡
አሳዎቹ፤ “ለሁሉም ጊዜ አለው፡፡ ለማረስም፤ ለመዝራትም፤ ለማጨድም ጊዜ አለው” የሚለው የተፈጥሮ ህግ (እውነት) አልገባቸውም፤ የአሁኗ ቅጽበት ላይ ብቻ ነው ያተኮሩት። በዚያ ላይ፤ ለማደግም ሆነ ለመፍጠን፤ አስፈላጊ የሆኑ ዋና ዋና ነገሮች አሉ፡፡ ለምሳሌ ውሃ፤ አፈርና ማዳበሪያ ሊያገኝ የሚችል ጠንካራ ስራስር፤ እንዲሁም የፀሐይ ብርሃንን መቀበል የሚችል ጤናማ ቅጠል፡፡ አሳዎቹ ግን፤ በቁንጽል የተክሎቹ ግንድ መርዘምን ብቻ ነው የፈለጉት፡፡
አሳዎቹ፤ እንዲህ ራሳቸውን የቅፅበታዊነትና የቁንፅልነት እስረኛ በማድረግ፤ ተክሎቹን ወደ ላይ በመጎተት እድገታቸውን ለማፍጠን ሞክረዋል፡፡ ዘዴያቸው፤ ለጊዜው የሰራ ቢመስልም፤ የተክሎቹ እድገት አልፈጠነም፡፡
የተክሎቹ ስራስር ተጎድቶ እድገታቸው ተገታ፡፡ ይህም ብቻ አይደለም፤ ጭራሽ ተክሎቹ ጠውልገው መሞት ጀመሩ - በማያዛልቅ ጥገና ወደ ባሰ ውድቀት፡፡
አንዳንዶቹ አሳዎች፤ የፀሐይ ሃሩር ሲያስቸግራቸው፤ ሃሩሩን ተቋቁመው ወይም የፀሐይ መከላከያ ባርኔጣ በመጠቀም፤ ተክሎቹ ፀሐይ ሊያገኙ በሚችሉበት ማሳ ላይ ለመትከል አልመረጡም። ተክሎቹ አፈር ላይ መተከላቸውን ብቻ በቁንጽል በማየት፤ ዛሬ ከሃሩር ማምለጣቸውን ብቻ በመመልከት፤ ዋሻ ውስጥ ለመትከል ሄደዋል፡፡ ግን የሚያዛልቅ አልነበረም፡፡ ተክሎቹ ጠወለጉ፤ ረሃቡም ከፋ፤ በየእለቱ ምግብ ፍለጋ በፀሐይ ሲንቃቁና በሃሩር ሲጠበሱ ይውላሉ፡፡
ረሃባቸውን በቅፅበት ለማሸነፍ ጓጉተው፤ የወዳደቁ ነገሮችን ለቃቅመው የበሉ አሳዎች፤ ለጊዜው ረሃባቸው የታገሰ ቢመስልም፤ ወዲያው ታመሙ፡፡ ረሃብን የሚያስታግስ ምግብ ለመፈለግ እንኳ መንቀሳቀስ አቃታቸው፡፡ የማያዛልቅ ከሻፊ ጥገና (የደመነፍስ መፍትሄ) በውድቀት ነው የሚቋጨው፡፡ ለዚህም ነው፤ የዛሬ ‹‹ችግሮች››፤ ትናንት ‹‹መፍትሄ›› የነበሩ ናቸው የሚባለው፡፡ የማያዛልቁ መፍትሄዎች፤ ችግርን ያስከትላሉ፡፡   

  በዲሲቲ  ኢንተርቴይመንትና ኤቨንትስ የተዘጋጀውና ከ500 በላይ የአገር ውስጥና የባህር ማዶ አምራቾችና ነጋዴዎች የሚሳተፉበት “አሲና ገና” የተሰኘው የገና ኤክስፖና ባዛር በዛሬው ዕለት የሚከፈት ሲሆን፤ እስከ ታህሳስ 28 ቀን 2015 ዓ.ም  በኤግዚቢሽን ማእከል ይካሄዳል፡፡
“አሲና ገና” 2015 ኤክስፖና ባዛር፤ የተለያዩ ሸቀጦች ለሸማቾች የሚቀርቡበት የንግድ ትርኢት ሲሆን በየዕለቱ በ10ሺ ሰዎች ይጎበኙታል ተብሎ የሚጠበቅና ከፍተኛ የንግድ ልውውጥና ግብይት የሚካሄድበት ዓመታዊ ባዛር ነው ተብሏል። ለ21 ተከታታይ ቀናት በሚዘልቀው በዚህ የንግድ ትርኢት፣ ከ50 በላይ አንጋፋና ወጣት ተወዳጅ ድምጻውያን የሚሳተፉበት የሙዚቃ ኮንሰርት የሚቀርብ  ሲሆን በተጨማሪም ታዳሚውን ባለእድል የሚያደርጉ እጣዎችና አጓጊ ሽልማቶች መዘጋጀታቸው ታውቋል፡፡ በትርኢቱ የወላጆችና ህጻናትን ፍላጎት  የሚያሟሉ የተለያዩ መዝናኛዎችና ጌሞችም እንደተካተቱ ተነግሯል፡፡

Saturday, 10 December 2022 13:36

ከሶሻል ሚዲያ በጨረፍታ

    ሰሜን ኮሪያውያን ለልጆቻቸው “ቦምቡ፣ ሽጉጤ” እና መሰል ስሞችን እንዲያወጡላቸው ታዘዙ


       ሰሜን ኮሪያ፣ ወላጆች፣ የልጆቻቸውን ስም የሀገር ፍቅርን በሚያንፀባርቅ መልኩ እንዲያስተካክሉ አዘዘች። የሀገር ፍቅርን ያንፀባርቃሉ የተባሉት ስሞች ግን “ቦምብ”፣ “ጠመንጃ” እና መሰል ወታደራዊ ትርጉም ያላቸው ናቸው።
ፒዮንግያንግ ከዚህ ቀደም የመጨረሻ ፊደላቸው ለስለስ ያሉ ስሞችን መጠቀም ፈቅዳ ነበር። በዚህም እንደ ኤሪ (ተወዳጅ ወይም ፍቅር የሚል ትርጉም ያለው) እና ሱ ሚ (የውብዳር ወይም ውበቱ) የሚሉና ፍቅርና ውበትን የሚገልፁ ስሞች በብዛት ጥቅም ላይ ሲውሉ ታይቷል።  አሁን ግን የሀገሪቱ መንግስት እነዚህ ስያሜዎች ጦር ጦር ሊሸቱ ይገባል ብሏል።
የሰሜን ኮሪያን ርዕዮተ አለማዊ አስተሳሰብና ወታደራዊ ዝግጁነት የማያሳዩ ናቸው የተባሉት ስሞችም በአዳዲስ አብዮታዊ ስያሜዎች ይቀየሩ ዘንድ ለወላጆች መመሪያ ተላልፏል ነው የተባለው።
የስም ለውጡ የልጆቹን ብቻ ሳይሆን የወላጆቻቸውን ወይም የአባታቸውንም ያካትታል። ወላጆች የስም ለውጡን የማያደርጉ ከሆነ ቅጣት እንደሚጠብቃቸውም ተነግሯል።
በአማራጭነት የቀረቡት ቹንግ ኢ (ሽጉጤ እንደማለት)፣ ፖክ ኢ (ቦምቡ ወይም ቦምቢት)፣ ኡይ ሶንግ (ሳተላይት)፣ ቹንግ ሲም (ታማኝ) እና የመሳሰሉት ይገኙባቸዋል፡፡
ለሬዲዮ ፍሪ ኤስያ አስተያየታቸውን የሰጡ አንድ የሀገሪቱ ዜጋ፥ “የሀገሪቱ መንግስት ያሳለፈውን የስም ቅያሬ በርካታ ሰዎች እየተቃወሙት ነው” ብለዋል። በተቀመጠው መመሪያ መሰረት ሁሉም ወላጅ የልጆቹን ስም ፖለቲካዊ ትርጉም እንዲኖረው እንዲያደርግ የተቀመጠው ቀነ ገደብ አንድ ወር ብቻ ቀርቶታል።
በርካቶችም ይህን የሰሜን ኮሪያ መንግስት ውሳኔ መቃወማቸውን ነው ስማቸው ያልተጠቀሰ የሀገሪቱ ዜጋ የተናገሩት። በደቡብ ኮሪያ ተወዳጅ የሆኑ ስሞችን መጠቀምም በጥብቅ ተከልክሏል፤ የምዕራባዊያንን ባህል እንደሚያንፀባርቁ በማመን።  
ሰሜን ኮሪያ ከዚህ ቀደምም ከቻይና፣ ጃፓን እና ደቡብ ኮሪያ የተወረሱ ናቸው ያለቻቸውን ስሞችን መጠቀም መከልከሏ ይታወሳል።  አሁን ደግሞ ርዕዮተ አለማዊ እሳቤዬን እና ወታደራዊ ዝግጁነቴን በስሞችም ካላየሁት እያለች ነው።
(አል ዐይን)

_________________________________________


                    ድህነቷን እናፍቀዋለሁ!
                      በድሉ ዋቅጅራ


        ኢትዮጵያ ድሀ የነበረች ጊዜ - ያኔ ያለው ለሌለው ያካፍል ነበር፤ የሌለው ጎዳና ወጥቶ፣ ደብር ተጠግቶ ለምኖ በልቶ ያድር ነበር፡፡ የድሀ ልጅ በባዶ እግሩ ትምህርት ቤት እየተመላለሰ ፊደል ይቆጥር ነበር፡፡ በኩራዝ ጭለማ ይረታ ነበር፡፡ . . . . ያኔ ነብስ ካወቅን ጀምሮ የሀገራችን ከድህነት መውጣት ያሳስበን ነበር፡፡ ወጣት ሆነን ሀገራችንን ከድህነት ለማውጣት እድገት በህብረት ዘመትን፣ መሰረተ ትምህርት ዘመትን፤ ሰላም እንድትሆን በብሄራዊ ውትድርና አገልግሎት ዘመትን፡፡
በወጣትነቴ ጠመንጃ ይዤ ዘብ የቆምኩላት ሀገር፣ ዛሬ በጎልማሳነቴም ሰላም አለማግኘቷ ልቤ ድረስ ይጠዘጥዘኛል፡፡ ድህነቷንም እናፍቀዋለሁ፤ ድሀ ለምኖ የሚበላበትን፣ አባወራ ጥጥ ለቀማ ቆላ የሚወርድበትን፣ ‹‹ግፋ ቢል አዶላ!›› ብሎ ወርቅ ቁፋሮ በቀን ሰራተኝነት የሚሰደድበትን፣ . . . . ድህነቷን እናፍቀዋለሁ፤ ሊያሳስበኝ ግን ልቦናዬ ጊዜ የለውም፡፡
ህይወት ረከሰ፤ ሞት ነገሰ፡፡ ከእንቅልፌ የሚቀሰቅሰኝ የወፎች ዜማ ሳይሆን የሞት ዜና ነው፡፡ በድህነት ያለፉት እናትና አባቴ ሰው ተሰቅሎ ሲሞት አይተው ለሳምንታት እንቅልፍ አይተኙም ነበር፡፡ የእኔ ዘመን አገዳደል ያኔ አልነበሩም፤ የሀገሬ ልጆች ከዚያ ወዲህ ተጠበው የደረሱባቸው የጭካኔ  ፍሬዎች ናቸው፡፡ ከእንቅልፌ ስነቃ ስለምሰማው ሞት ሳስብ ውዬ ስለእሱው ሳስብ ያሸልበኛል፡፡
በየት በኩል ስለሌላ ነገር ማሰብ ይቻላል! የሀገሬ መልክ ሆኖ የሚያሳስበኝ ሞት እንጂ ድህነት አይደለም፡፡ ስለሞት ባሰብኩ ቁጥርም በልጅነቴ የኖርኩት ሰላማዊ ድህነቷ ይናፍቀኛል። ሞት በሚዘመርባት ሀገሬ ውስጥ እየኖሩ፣ ከድህነት ሊፈውሷት የሚጥሩ ዜጎቿን ልረዳቸው አቅቶኛል፡፡ እኔ ግን እላለሁ! ኢትዮጵያ ከድህነቷ የምትወጣው ማለቂያ በሌለው የዜጎች ሞት ከሆነ፣ ለዘለአለም ድሀ ሆና ትኑርልን፤ እንኑርባት፡፡

_______________________________________
 
                  “ዛሬም ኢትዮጵያ ትፈተናለች እንጂ አትፈርስም”


        “--የእያንዳንዳችን ችግር ሊፈታ የሚችለው የሁላችንም ችግር ሲፈታ ነው፣ በተናጠል የራሱን ችግር ብቻ መፍታት የሚችል ማንኛውም ግለሰብና ቡድን ከኢትዮጵያ ችግር በፊት ቀድሞ የሚፈታ የሰፈር ችግር እንደሌለ መገንዘብ አለበት-- በዚህ ቀን የሁላችን ባህል፣ ታሪክ ቅርስ፣ እሴት፣ የኢትዮጵያ ሃብትና የጋራ ኩራት ሆኖ የሚታይበት፣ ሁላችንም ለኢትዮጵያ እጅግ አስፈላጊ መሆናችንና ውበታችን በኢትዮጵያ ጥላ ስር ጎልቶ የሚታይና የምንማርበት ዕለት ነው--፡፡
ሀገር በቤት ይመሰላል፥ ማገሩ፣ ወራጁ፣ ጣራው ተሰናስለው ቤት እንደሚሆኑ ሁሉ ሁሉም ብሔሮችና ብሔረሰቦች እያንዳንዳቸው ሰበዝ ሆነው ሲደመሩ ታላቋንና ውቧን ኢትዮጵያ ያሳያሉ፡፡ -- ስለሆነም በተናጠል ጎልተን ለመታየት ሳይሆን በጋራ ለማበብ ልባችን የቀና አዕምሯችንም የሚያስተውልና የሚያሰላስል ሊሆን ይገባል--፡፡ ትናንትና ያለፈና ያመለጠ ታሪክ ነው፣ ትናንትን ለመማሪያ ብቻ መጠቀም ከቻልን ነጋችን ያማረ ይሆናል፤ ዛሬ የትናንትን ጉዳይ እያነሳን ብንወቅስና ብናወድስ ሰዎቹ የሉምና አይሰሙንም፤ ትርጉምም የለውም--፡፡ እኛ መልካም ነገን ለልጆቻን ለመገንባት ከትናንት መማር አለብን፤ መጪው ትውልድ ከልመና የተላለቀና የተማረ እንዲሆን መገፋፋቱንና መጠላላቱን መተው ይገባል፡፡
በኢትዮጵያ ውስጥ ከግራ ከቀኝ ዋልታ የረገጡ እሳቤዎች አሉ፤ ከትናንት እሳቤ ያልተላቀቁ፣ ነገ የሚሰራበትን እያንዳንዱን ብሎኬት የሚያፈርሱ፤ በጋራ መኖር ሳይሆን መገፋፋትን የሚመርጡ፣ በሌሎች አጀንዳ የተገዙ፣ በንጹሃን ደም ፖለቲካ የሚሰሩ ጥቂት ግለሰቦችና ቡድኖች እንዲሁም የሚዲያ ሰዎች አሉ፡፡ --ለእነዚህ ጊዜውን ለሳቱ ወንድሞቻችንን ያለኝ ምክር፣ ዛሬም ኢትዮጵያ ትፈተናለች እንጂ አትፈርስም የሚል ነው፡፡ -- የኢትዮጵያ ብልጽግናና ልዕልና የሚመነጨው ከእውነትና ፍቅር ነው፤ በአንጻሩ የተሸናፊ ሃይሎች አጀንዳ ጥላቻ፣ ግድያና መገፋፋት፤ ንጹሃንን ማጎሳቆል ነው።  ከግራም ከቀኝም ያሉ ዋልታ የረገጡ እሳቤዎች  ለኢትዮጵያ ስለማይበጁ ሁሉም ኢትዮጵያዊ ለአጀንዳዎቹ ጀሮ መስጠት የለበትም፡፡--”
(ጠ/ሚኒስትር ዐቢይ አህመድ ህዳር 29 ቀን 2015 ዓ.ም የብሔር ብሔረሰቦችን
ቀን  አስመልክቶ በአዋሳ ካደረጉት ንግግር የተወሰደ፡፡)

____________________________________


                   በዘንድሮው የቢቢሲ ተፅእኖ ፈጣሪ መቶ ሴቶች ዝርዝር ውስጥ የተካተቱት ኢትዮጵያውያን


        ቢቢሲ በዓለማችን ላይ ተደማጭነት ያላቸው፣ ተፅእኖ ፈጣሪ የሆኑና  ድምፃቸውን ለሰብዓዊነት እያዋሉ ያሉ መቶ ሴቶችን በየዓመቱ ይመርጣል። የዘንድሮውን መቶ ሴቶች ዝርዝርንም ከሰሞኑ ይፋ አድርጓል።
በዘንድሮው  ዝርዝር ውስጥ ኢትዮጵያውያኖቹ የራይድ መሥራች ሳምራዊት ፍቅሩ እንዲሁም በትግራይ ጦርነት ለተጎዱ ሴቶች ከፍተኛ ድጋፍ በማድረግ ላይ የምትገኘው ወጋሕታ ገብረዮሐንስ ተካትተውበታል።
የኮምፒውተር ፕሮግራመሯ ሳምራዊት ፍቅሩ፣ምንም እንኳን እስከ 17 ዓመቷ ድረስ ኮምፒውተር ተጠቅማ ባታውቅም፣  ከራይድ የታክሲ መተግበሪያ ጀርባ ካሉት ኩባንያዎች መካከል አንዱ የሆነው የሃይብሪድ ዲዛይን መሥራች ነች። ከሥራ አምሽታ ታክሲ ለመያዝ ደኅንነት ስላልተሰማት እንዲሁም፣ ከሾፌሮች ጋር ይህንን ክፈይ በሚል የማያቋርጥ ጭቅጭቅ ውስጥ መግባት ስላታከታት ይህንን መተግበሪያ እንደፈጠረች ትናገራለች።  ሳምራዊት ሥራውን ስትጀምረው የነበራት መነሻ ካፒታል ከሁለት ሺህ ዶላር ያነሰ ነበር። በአሁኑ ወቅት ኩባንያዋ በርካታ ሴት ሠራተኞችን ቀጥሯል።
በኢትዮጵያ የቴክኖሎጂ ኢንዱስትሪ ውስጥ ያሉት ሴቶች ጥቂት ሲሆኑ፣ ሳምራዊት የመጪውን ጊዜ ሴት ሥራ ፈጣሪዎችን ማነሳሳት ትፈልጋለች።
“ሴቶች በባለቤትነት የሚቆጣጠሯቸው ማዕከላት በቁጥር እያደገ ነው። በአሁኑ ወቅት ወጣት ሴቶች የፈጠራ ሀሳቦቻቸው እውን እንዲሆኑ ገንዘብ የሚያገኙበት መንገድ ሊመቻችላቸው ይገባል” ትላለች፡፡
የሰብአዊ እርዳታ ሠራተኛ የሆነችው ወጋሕታ ገብረዮሐንስ፣ በትግራይ ጦርነት ምክንያት የተፈጠረውን የተመጣጠነ ምግብ እጥረት ለመቅረፍ ያለመ “ህድሪና” የተባለ ለትርፍ ያልተቋቋመ ድርጅት መሥራች ናት። ህድሪና በጦርነት የተጎዱ ሴቶችንና ህጻናትን ለመርዳት በርካታ ፕሮጀክቶችንም ነድፎ እየተንቀሳቀሰ ይገኛል። ከእነዚህም መካከል በአገር ውስጥ ተፈናቅለው በየመጠለያዎቹ  ለሚገኙ  የምገባ ፕሮግራምና የከተማ አትክልት ማልማት  ይገኙበታል።
ድርጅቱ በጦርነቱ የተደፈሩ ሴቶችን ድጋፍ ከመስጠት ባሻገር  በትግራይ በጦርነቱ ወቅት  በተጣለው እገዳ የተነሳ ሕይወታቸውን ለማቆየት ወደ ወሲብ ንግድ ከገቡ ሴቶችም ጋር በተያያዘ የተለያዩ ፕሮጀክቶች አሉት።

_____________________________________________


                     ለኢትዮጵያ ሀገሬ፦
                       ሙሼ ሰሙ


          የገደለው ባልሽ፤ የሞተው ወንድምሽ
ሀዘንሽ ቅጥ አጣ፤ ከቤትሽም አልወጣ
ፖለቲካዊና ኢኮኖሚያዊ ፍላጎትን በግድ ለመጫን ሲባል አቅመ ደካሞችን፣ ሴቶችንና ሕጻናትን ጨፍጨፎ ቅዠቱኝ ማሳካት የቻለ ሕዝባዊ ትግል የለም። የጠራ ሕዝባዊ አጀንዳ ያለው፣ በበሰለ ፖለቲካዊና ኢኮኖሚያዊ አስተሳሰብ ዙርያ የተሰባሰበና የተደራጀ የነጻነትና የመብት ታጋይ በሌሎች ጭቁን ሕዝቦች ላይ በግፍ እጁን አያነሳም።
በዛው ልክ፣ የትም አካባቢ የሚገኝ ጭቁን ሕዝብ በሌላው ጭቁን ሕዝብ ላይ ግፍ በመስራት ነጻነቴንና መብቴን አረጋግጣለሁ፣ ትግሌንም ከግብ አደርሳለሁ ብሎ አያምንም።
የጠላቴ ጠላት በሚል የጅምላ ፍረጃና ዘርን በማጥራት ሰበብ የሚካሄድ ግፈኝነት፣ ዛሬ የጋራ ጠላቴ የሚለውን ሲጨርስ ነገ ደግሞ በጅምላ የኔ ናቸው ወደ ‘ሚላቸውና የሞራል ከለላና ሽፋን ወደ ሰጡት በመዞር የእናትና የአባት የዘር ግንዳቸውን እያሰሰ፣ የሐይማኖት መሰረታቸውን እየመረመረ፣ የትዳር ጓደኛቸውን ዘር እየመነዘረ፣ እነሱም እንደሚበላቸው ከታሪክ መማር ይገባል።
ለየትኛዎቹም ዓይነት ግፈኞች የነፍስ አድን ትርክት የመቀመር አባዜ የመጨረሻ ውጤቱ፣ እጅን በእጅ የመብላት ያህል የዜሮ ድምር ስሌት ነው።

_________________________________________


                  የእኛ የኢትዮጵያውን ቀን መቼ ነው???


       አገራችን ኢትዮጵያ ከጊዜ ወደ ጊዜ ትሻሻላለች ብለን ብንጠብቅም ነገሮቿ እየባሱ የልጆቿ ችግሮች እየጠኑ፣ ኑሯችን እየከበደና የዜጎች የመኖር መብት እየተጣሰ፣ ከተማና መንገድ ማስዋብን ግንባታን አጠንክረን እየሰራን በግማሽ እየኖርን አለን!!!
ይሄ በየዓመቱ የሚከበረው የብሔር ብሔረሰቦች ቀን ሁሌም ይደንቀኛል። ከዚህ በላይ እንደ አገር የምናገኘው እድል መኖሩን እጠራጠራለሁ፡፡ ህዝባችንን አንድ ለማድረግ ሁሉም የሚታቀፍበት “የኢትዮጵያ ቀን” ብለን ሰይመን፣ በብሔር ብሔረሰባችን አልባሳት ተውበን፣ (ባህላችንን እያስተዋወቅን) በመንገድ ላይ ስንሄድ፣ ወዴት ልትሄድ ነው ስንባል “የኢትዮጵያን_ቀን” ላከብር ብለን አገራችንን መጥራት፣ አንድነታችንን ማሰብ ስንችል፣ በጎጥ የሚያኖረንን፤ እያጋደለን ያለውን ብሔር ብሔረሰቦች ብለን የመቧደን ቀንን እናከብራለን።
የእኛ ቀን የታለ? እኛ በሰዎች (በዜጎች) እኩልነት የምናምን፣ በአንድ ኢትዮጵያ ውስጥ ተከባብረን ተነጋግረን ተስማምተን መኖር የምንፈልገው ኢትዮጵያውያን ቀናችን መቼ ነው? በእኛ አይምሮ በአገር ብሔር ይጠራል እንጂ፤ በብሔር አገር አይጠራም!!!
ኢትዮጵያዬ ቀንሽ መቼ ነው???
(ሰናይ ኢትዮጵያ)

 - ኳታር በኢትዮጵያ የዓይን ህክምና ፕሮጀክቶችን እየደገፈች ነው
     - በኳታሩ አሚር ስም የኩላሊት ህክምና ሆስፒታል ይገነባል

    በኳታር የኢትዮጵያ ልዩ መልዕክተኛና ባለሙሉ ስልጣን አምባሳደር የሆኑትን አቶ ፈይሰል አሊዬን በኳታር የሚገኘው የአዲስ አድማስ ጋዜጠኛ ግሩም ሰይፉ አነጋግሯቸዋል።
          


           “በዲፕሎማሲው ዓለም ከ18 ዓመት በላይ ሰርቻለሁ”
ኳታር ከመምጣቴ በፊት  በዲፕሎማሲው ዓለም ከ18 ዓመታት በላይ ልምድ አለኝ፡፡ የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር የገባሁት በ1997 ዓ.ም ነው፡፡  በውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ቆይታዬ፤ በተለያዩ የውጭ አገራት ያሉ ኢትዮጵያውያኖችና ትውልደ ኢትዮጵያኖችን  ከአገራቸው ጋር ለማስተሳሰር፤ በሚኖሩበት አገር መብታቸውና ጥቅማቸው እንዲከበር ለማድረግ የሚያስችል  አንድ የስራ ክፍል አለ፡፡ የዲያስፖራ ተሳትፎ ጉዳዮች ዲያሬክቶሬት ጀነራል ይባላል። በዚያ ዲፓርትመንት ውስጥ በዲያሬክተርነትና በዲያሬክተር ጀኔራልነት አገልግያለሁ፡፡ ከዚያ በፊት በሚኒስትር ቆንስላነት ደረጃ በዋሽንግተን በሚገኘው የኢትዮጵያ ኤምባሲ ለአምስት አመታት ሰርቻለሁ፡፡ ከዚያ ከተመለስኩ በኋላ ለአራት አመታት በውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር የዲያስፖራ ጉዳዮች ዲያሬክተር ሆኜ ነው ያገለገልኩት፡፡ በአጠቃላይ አሁን የምናየው የዲያስፖራ ፖሊሲ ቀረፃ፤ የዲያስፖራ ተሳትፎ ስትራቴጂና የተለያዩ ፕሮግራሞች ላይ በስፋት ተሳትፈናል፡፡ በውጭ አገር ያሉ ዲያስፖራ ኢትዮጵያውያንና ትውልደ ኢትዮጵያውያን ቁጥራቸው እጅግ በርካታ ነው፡፡ በትክክል ተቆጥሮ የታወቀ ባይሆንም በግምት ከ3 ሚሊዮን በላይ ይሆናል፡፡ ይህ ቁጥር ከብዙ አገራት የህዝብ ብዛት የላቀ ነው፡፡ ለምሳሌ ኳታር 400 ሺ ዜጎች ነው ያሏት፡፡ ከበርካታ አገራት ህዝቦች  በቁጥር የሚበልጡ ብቻ ሳይሆን የተለያየ ክህሎት፤ እውቀትና ልምድ ያላቸው ናቸው፡፡ ብዙዎቹ በምዕራባውያን አገራትና በመካከለኛው ምስራቅ በተለያየ የስራ ሃላፊነት ላይ ተሰማርተው ይገኛሉ። በአፍሪካ አገራትና በጎረቤት አገሮችም የሚኖሩ አሉ። በመላው ዓለም ተበትነው ሲኖሩ በአብዛኛው ህይወት የሰጠቻቸውን እድል የሚጠቀሙም ቢሆን፤ በእውቀታቸው በጉልበታቸውና በሙያ ልምዳቸው የሚሰሩ ቁጥራቸው በርካታ ነው። ይሄን እውቀት፤ ልምድና ሰርተው ያገኙትን ሃብት ለአገራቸው ቢያመጡት፣ ለዜጎቻቸው የተሻለ የስራ እድል ይፈጥራሉ፡፡ ያ ብቻ ሳይሆን ያገኙትን ልምድና እውቀት አገራቸውን ለመለወጥ ሊጠቀሙበት ይገባል ወይንም በዚያ ተግባር ላይ ማዋል ይኖርባቸዋል፡፡ በዚህ ድርጊታቸውም እነሱም ተጠቃሚ ይሆናሉ፡፡ እኛ የማልማት አቅማችን ትልቅ ነው፡፡ ይሄንን ወደ ልማት ወደ ሃብት የሚቀይር የፋይናንስ አቅም ከመጣ አገራችንን በፈጠነ ሁኔታ ማሳደግ እንችላለን፡፡ የዲያስፖራው ፖሊሲ አንዱ ትኩረት፤ የዲያስፖራውን አቅም፤ እውቀቱን ጉልበቱንና ልምዱን እንዲሁም በተለያዩ አገራት ያገኘውን ሃብቱን ለአገሪቱ ልማት በማዋል፣ ራሱም ተጠቃሚ በመሆን እንዲሰራ ዕድል መፍጠር ነው፡፡ ሌላው ጉዳይ በተለያዩ የውጭ አገራት ሲኖሩ ጥቅማቸው የሚጎዳበት መብታቸው የሚጣስበት ሁኔታ አለ፡፡ የሚኖሩበትን አገር ህግና ስርዓት ጠብቀው እስከሰሩ ድረስ የእነሱ መብትና ጥቅም መከበር አለበት፡፡ መብትና ጥቅማቸው ተጥሶ ሲገኝ በየአገሩ ያለው ኤምባሲ አንዱ ትልቁ ስራው ይህን ማስከበር ነው፡፡ ከዚህ አኳያ በውጭ  ጉዳይ ሚኒስቴር የዲያስፖራ ጉዳዮች ላይ ስንሰራ፤ ዲያስፖራው እንደ አንድ የልማት አቅም እንዲታይ ብዙ ስራዎች ተከናውነዋል፡፡ የእኔ የስራ ልምድ ከዚህ ጋር የተያያዘ ነው፡፡ በመካከለኛው ምስራቅ ለኢትዮጵያውያን የስራ እድል ያለውን ያህል የሚበደሉበትም ሁኔታ አለ፡፡ ስለዚህ ዜጎች ያሉትን እድሎች እንዲጠቀሙ፤ ሲበደሉ ደግሞ መብታቸው እንዲከበር የማድረግ  ስራዎች ላይ ትኩረት በማድረግ በሳውዲ አረቢያ ከ2015 እስከ 2017 ዓ.ም ሰርቻለሁ፡፡ ከዚያም እስከ 2020 ዓ.ም በኳታር ከሰራሁ በኋላ ወደ ኢትዮጵያ ተመልሼ በውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር በፕሮቶኮል ጉዳዮች ዲያሬክተር ጀነራልነት እስከ 2022 ዓ.ም ድረስ  ሰርቻለሁ፡፡ ከ6 ወራት በፊት ጠቅላይ ሚኒስትር ዶክተር ዐቢይ አዳዲስ አምባሳደራትን ሲሾሙ ነው ወደ ኳታር ተመድቤ የመጣሁት፡፡
የውጭ ጉዳይ ፖሊሲ ሪፎርም
ተሃድሶው እጅግ በጣም አስፈላጊ ነው። ምክንያቱም የውጭ ግንኙነት  ስራችን ዋና አላማ እንደ ሃገር ብሄራዊ ጥቅማችንን ማስከበር ነው፡፡ ብሄራዊ ጥቅም በብዙ መልኩ ይገለፃል። የመጀመርያው ከአገራት ጋር ያለን ግንኙነት በፖለቲካው፤ በማህበራዊ ትስስሩ፤ በህዝብ ለህዝብ፤ በኢኮኖሚው፣ በዲፕሎማሲው… በሁሉም መስክ  ጥቅም መምጣት አለበት፡፡ ግንኙነት  ከፈጠርንበት አገር ጋር ሊኖር የሚችለውን ኢኮኖሚያዊ ፋይዳ ማሳደግ ያስፈልጋል፡፡ ሌላው የዜጎች መብትና ጥቅም የሚከበርበት ሁኔታ ነው። በሌላ በኩል የአገር ገፅታ ግንባታም አለ፡፡ ሁሉም አገር በዲፕሎማሲው በሰራው ልክ ገፅታው ይገነባል፡፡
ኢትዮጵያ ሃብታም አገር ስላልሆነች ከሚገኘው ጥቅም ጋር ዲፕሎማሲውን ማስተሳሰር ያስፈልጋል። የውጭ ግንኙነታችን ትልቁ ትኩረት ከጎረቤት አገራት ይጀምራል፡፡ ኢትዮጰያ የባህር በር የሌላት አገር እንደሆነች ይታወቃል፡፡ ይህን የባህር በር አገልግሎት የምናገኘው ከጎረቤቶቻችን  ነው። ስለዚህም ከአገራቱ ጋር የጠበቀ የዲፕሎማሲ ትስስር ያስፈልገናል፡፡ ጎረቤት ላይ የተፈጠረ ችግር አንተም ዘንድ ይደርሳል፡፡ አንተ ጋ የተፈጠረ ችግርም ጎረቤት ዘንድ ይደርሳል፡፡ ስለዚህም ጎረቤት ሆነን እስከተፈጠርን ድረስ በሁሉም መስክ ተባብረን መስራት አለብን፡፡ ጎረቤቶቻችን በሰላም ማደራቸው ሰላም መሆናቸው፤ የእኛ ሰላም መሆን ነው፡፡ በዚያ ውስጥ የኢትዮጵያን ጥቅም ማስጠበቅ ግን ይኖርብናል፡፡ ከዚህ አኳያ ሁሉም የምናደርጋቸው ዲፕሎማሲዎች  ከአገራችን ጥቅም አንፃር የተቃኙ መሆን አለባቸው፡፡ እያንዳንዱን አገር የምንቀርበበትን መንገድ በደንብ ማየት መተንተን፤ ለዚያም የሚያስፈልግ የሰው ሃይል አደረጃጀትና በጀት የመመደብ ሁኔታ ወሳኝ ነው፡፡
ዋናውና ትልቁ የውጭ ጉዳይ ፖሊሲ አጠቃላይ ሪፎርም በዚህ አቅጣጫ ነው። ተሃድሶውን ስንሰራው ከሆነ አገር ጋር ያለን የዲፕሎማሲ ግንኙነት በምን ደረጃ  ላይ እንደሚገኝ ያስቀምጣል። ስለዚህም ለጎረቤቶቻችን ከፍተኛ ትኩረት እንሰጣለን፡፡ ከየክፍለ አህጉሩ ከፍተኛ ተፅዕኖ ያላቸውን አገራትም ዲፕሎማሲያችን ይመለከታል። ከመካከለኛው ምስራቅ አኳያ በተለይ የዜጎቻችንን መብትና ጥቅም ለማስጠበቅ ነው የምንሰራው፡፡ ህዝባችን ወደዚህኛው የዓለም ክፍል በህጋዊና  ህጋዊ ባልሆነ መንገድ እንደሚፈስስ ይታወቃል፡፡ በተደራጀ  ህገወጥ የሰዎች ዝውውር ለበርካታ የአዕምሮ፤ የስነልቦናና የፋይናንስ  ጉዳት የሚዳረጉ ወገኖቻችን ጥቂት አይደሉም። ወደ መካከለኛው ምሥራቅ ከሚሰደዱት ዜጎች መካከል ለአዕምሮ፤ ለስነልቦናና  ለአካል ጉዳት የሚዳረጉ አሉ፡፡ ጥቂቶቹ በስነልቦና ተጎድተውም ቢሆን የፈለጉት ቦታ ይደርሳሉ፡፡  ብዙ መከራ ደርሶባቸው ራሳቸውን የሚያጠፉ ዜጎችም አሉ፡፡ ይህን ለማስቆም በመካከለኛው ምስራቅ የዜጎችን መብትና ጥቅም ለማስከበር መስራት ያስፈልጋል፡፡
 በሌላ በኩል፤ በመካከለኛው ምስራቅ የሚገኙ አገራት የኢንቨስትመንት አመንጪዎች ናቸው። ሁሉም ባይሆኑም የየራሳቸው የኢንቨስትመንት አቀራረብና ሃብት አላቸው፡፡ ያንን ሃብት አገራችን ላይ ኢንቨስት እንዲያደርጉት እንሰራለን፡፡ ሶስተኛው ትኩረት የቱሪዝም አመንጪ አገራት መሆናቸውን ከመገንዘብ የሚመጣ ነው፡፡ ቱሪስቶች ከመካከለኛው ምስራቅ ተነስተው ወደ አውሮፓና ሩቅ ኤሽያ እየሄዱ ናቸው፡ ለእነሱ ምቹ የሆነ አመቺ የቱሪዝም መሰረተ ልማት በመገንባትና መስተንግዶዎችን ጨምሮ ሁኔታዎችን ካመቻቸን ካላቸው የቱሪዝም አቅም የተወሰነውን መውሰድ እንችላለን፡፡ በጠቅላይ ሚኒስትራችን የተገነቡና የተጀመሩ ትልልቅ የቱሪዝም መዳረሻዎች መኖራቸውን እናውቃለን፡፡ አዲስ አበባ ብቻ ሳይሆን ክልሎችም ለቱሪዝም ትኩረት ሰጥተው እየሰሩ ናቸው፡፡ በርካታ ቁጥር ያላቸው የመካከለኛው ምስራቅ ቱሪስቶች ኢትዮጵያን መዳረሻ እንዲያደርጓት መስራት ያስፈልጋል፡፡
ከኳታር አኳያ በተጨማሪነት የምንሰራበት ጉዳይ አለ፡፡ ኳታር የታዋቂው ዓለም አቀፍ ሚዲያ አልጀዚራ መቀመጫ እንደሆነች ይታወቃል፡፡ ከአልጀዚራ ጋር በሚዲያው ዘርፍ በመተባበርና ሚዲያው በመካከለኛው ምስራቅ ያለውን ተፅእኖ በመጠቀም፤ የአገራችንን መልካም ገፅታ ለመገንባት መስራት ይቻላል፡፡ ለአገራችን የሚዲያ ተቋማት የልምድ ልውውጥና የሙያ ስልጠናዎችን ማግኘት እንችላለን፡፡ ከላይ የዘረዘርናቸውን የትኩረት አቅጣጫዎች ለመፈፀም የሚያስችል ሪፎርም ነው፤ በዲፕሎማሲው መስክ የተደረገው፡፡ በተለይ አሁን ያለው አለም አቀፋዊ ተለዋዋጭ ሁኔታ ጋር ውጭ ግንኙነት ስራችን  ይያያዛል፡፡ያንን የሚመጥን የውስጥ ተቋማዊ ፍተሻነው የተደረገው፡፡
የኢትዮጵያና ኳታር ዲፕሎማሲያዊ ግንኙነት
የኳታርና የኢትዮጵያ የሁለትዮሽ ግንኙነት አሁን ባለው ሁኔታ እጅግ በጣም ጥሩ ነው። በዓለም አቀፍ መድረኮች እንተባበራለን፡፡ አሁን ያሉት የኳታር አሚር የኢትዮጵያን ሁኔታ ይከታተላሉ፡፡ አባትየው ሼክ አህመድ ቢን ካሊፋም እንደዚያው ናቸው፡፡ የኳታር መንግስት፤ አሚሩ ኢትዮጵያን ጎብኝተዋል፡፡ በተመሳሳይ የቀድሞው ጠቅላይ ሚኒስትር ሃይለማርያም ደሳለኝ ቀጥሎ ደግሞ ጠቅላይ ሚኒስትር ዶክተር ዐቢይ አህመድ በ2019 ላይ ኳታርን ጎብኝተዋል፡፡  በከፍተኛ የአገር መሪዎች ደረጃ የሚደረጉ ጉብኝቶች የሁለቱን አገራት የዲፕሎማሲያዊ ግንኙነት ደረጃን ያሳያሉ።  ጉብኝቱ ብቻ ሳይሆን ከጉብኝቱ ቀጥሎ የተሰሩ በርካታ ስራዎችም አሉ፡፡ በሁሉም መስክ ከ10 በላይ ስምምነቶችና ወደ 12 የሚደርሱ የመግባቢያ ሰነዶችን ተፈራርመናል- በሚዲያ፤ በትምህርት  በኢኮኖሚ፤ በንግድና፤ በግብርና ዘርፎች፡፡ ይህ ሁለቱ አገራት ዲፕሎማሲያቸውን የበለጠ ለማሳደግ ያላቸውን ፍላጎት ማሳያ ነው፡፡ በኳታር ለሚኖሩ ኢትዮጵያውያን በተለይ ለልጆቻቸው በራሳቸው ካሪኩለም እንዲማሩ እድል ተፈጥሯል። የቀድሞው ጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለማርያም ደሳለኝ፤ ለኳታሩ አሚር  ባቀረቡት ጥያቄ መሰረት ትልቅ ትምህርት ቤት ተሰጥቶናል፡፡ ይህ ትምህርት ቤት ሙሉ እድሳት ተደርጎለት፤ የውስጥ መሰረተ-ልማት ተሟልቶለት ነው የተሰጠን፡፡ ኳታር ላይ እንደዚህ አይነት እድል ያገኙ አገራት ጥቂት ናቸው። ምናልባትም ከአፍሪካ ሱዳንና እኛ እንደሆንን እገምታለሁ፡፡ ይህ የሚያሳየው  የሁለቱ አገራት የዲፕሎማሲ ግንኙነት ውጤታማ መሆኑን ነው፡፡ በኳታር እስከ 30ሺ የሚደርሱ ኢትዮጵያውያን ይገኛሉ፡፡ በተለያዩ የስራ መስኮች የተሰማሩ ናቸው፡፡ ከኳታር መንግስት ጋር የስራ ስምሪት ስምምነት አድርገናል፡፡ በዚያ ማዕቀፍ ውስጥ ኢትዮጵያውያን  የስራ እድል እንዲያገኙ ይደረጋል፡፡ ይህም የግንኙነታችን ሌላው ውጤት ነው፡፡ በኢንቨስትመንት ረገድ የፕሮሞሽንና የጥበቃ ስምምነት በኳታር በኩል አልቆ በኛ በኩል ሊረጋገጥ እየተጠበቀ ነው፡፡ ይህም በሁለቱ አገራት ዜጎቻቸው ኢንቨስት የሚያደርጉበትና ለኢንቨስትመንታቸው ጥበቃ የሚያገኙበት ዋስትና እንዲፈጠር፤ ከታክስ ነፃ የሚሆኑበት አሰራር እንዲዘረጋ ነው፡፡ የሁለቱም አገራት ዜጎች ኢንቨስት ካደረጉ ኢትዮጵያ ግብር ከከፈለ በኳታር እንዳይከፍል፤ ኳታር ግብር ከከፈለ በኢትዮጵያ እንዳይከፍል የሚያደርግ ነው። በአንድ ኢንቨስትመንት ሁለት ግብር እንዳይከፍሉ ማለት ነው።  የኢትዮጵያ ብሮድካስት ጋዜጠኞች በአልጀዚራ የሚዲያ ተቋም ስልጠና እንዲያገኙ ተደርጓል፡፡ የፋና እና ሌሎች የክልል ሚዲያ ተቋማትም በተመሳሳይ እድል እንዲጠቀሙ ሆኗል።  በጤናው ዘርፍ ኳታር  በኢትዮጵያ  የአይን ህክምና  ፕሮጀክቶችን በቀጥታም ሆነ በተዘዋዋሪ እየደገፈች ነው፡፡ በዚህ አቅጣጫ የመጀመርያውን ምዕራፍ ጨርሰን ወደ ሁለተኛው ምዕራፍ በመሸጋገር ላይ ነው የምንገኘው፡፡ በሂደት ላይ ያለው ደግሞ ልዩ የኩላሊት ህክምና ሆስፒታልን በኳታሩ አሚር ስም ኢትዮጵያ ላይ መገንባት ነው፡፡ ክእነዚህ በሻገር የምንተባበርበት ብዙ መድረክ አለ፡፡ የሁለትዮሽ ግንኙነት ብቻ አይደለም፡፡ ኳታር በብዙ ዓለም አቀፍ መድረኮች ላይ ንቁ ተሳታፊ ናት፡፡ ኢትዮጵያም በተመሳሳይ። የጋራ ጥቅማችንን ለማስከበር እንተባበራለን። በተባበሩት መንግስታት ኒውዮርክ፤ በጄኔቫ፤ በዓለም አቀፍ ሲቪል አቪዬሽን ላይ በእጩዎቻችን በውሳኔዎቻችን እንደጋገፋለን እንተባበራለን፡፡ በብዙ ዓለም አቀፍ መድረኮች የምንተባበርበት በመተማመን ላይ የተመሰረተ መልካም ግንኙነት አለን፡፡ ኢትዮጵያ በምንም አይነት በቲፎዞ አንድን አገር የምትደግፍበት ወይም የምትጠላበት ታሪክ የላትም፤ ሁሉንም አገራት በእኩል ዓይን ትመለከታለች፡፡ በመከባበር በመተባበር መንፈስ አብሮ መስራት ነው ፖሊሲያችን፡፡ ባለፈው የገልፍ ቀውስ ጊዜ  የተወሰኑ አገራት በኳታር ላይ ማዕቀብ ጥለው ነበር፡፡  የአንድ ወገን ቲፎዞ ሆነው የወጡ ብዙ አገራት ነበሩ። ኢትዮጵያ ያንን አቋም አልያዘችም፤ ገለልተኛ አይደለም የሆነችው፤ ችግራቸው እንዲፈታ ነው። ጥረት ያደረገችው፡፡ ክቡር ጠቅላይ ሚኒስትር ዶክተር ዐቢይ እዚህ በመጡ ጊዜ ከኳታሩ አሚር ሼክ ተሚም ጋር ባደረጉት ውይይት፤ ‹‹እናንተ አንድ ህዝብ ናችሁ፤ አንድ ባህል ያላችሁ አንድ እምነትና ስነልቦና ያላችሁ ናችሁ፤ ህዝባቻችሁ በጋብቻ የተሳሰረ ነው፤ ይህን ህዝብ አትለያዩ ሰላም ፍጠሩ፤ ለሰላም መስዕዋትነት መክፈል ካስፈለገ ክፈሉ፤ ይሄ ህዝብ እንደ ድሮ አብሮ እንዲኖር አድርጉ፡፡ ይህን በማድረግ ታሪክ እንዲያስታውሳችሁ ሥሩ›› ነው ያሏቸው፡፡ የውጭ ግንኙነታችን ዋነኛው መርህ፤ የጋራ መከባበር (mutual respect) ነው። ወገንተኛ ያለመሆን፤ ሁሉን አገር እንደ አገር ማክበር፤ ለሰላምና መረጋጋት አስተዋፅኦ ማድረግ ነው- መርሃችን እንደ አገር በዓለም ላይ በዚህ ደረጃ ነው መታየት  የምንፈልገው፡፡

   ከረዥም ጊዜ በፊት በተካሄደ ጦርነት ውስጥ ተሳትፈው ወደ መንደራቸው የተመለሱ ተዋጊዎች ስለ ጦርነቱ ሂደት ይወያያሉ።
አንደኛው፤
“ጠላት ባይቆርጠን ኖሮ አንሸነፍም ነበር!”
ሁለተኛው፤
“የለም፤ ትልቁ ችግር የደጀን ጦር በሰዓቱ ስላልደረሰልን ነው። የፊት አውራሪው ጦር በጣም ፈጠነ። አዛዣችን “ቅደሙ! ቅደሙ!” ባይል ኖሮ ጦሩ በአንድ ፍጥነትና ረድፍ ይገሰግስ ነበር።”
ሦስተኛው፤
“እኔ ደሞ የሚታየኝ ጦራችን ውስጥ ሰርገው የገቡ የጠላት ወገን ሰዎች መኖራቸው ነው! ተሸርሽረናል!”
አንደኛው፤
“አሁን ከመካከላችን ገብቶ ያኔ ያተራመሰን አንድ ሰው እንደዚያ ሊያምሰን የቻለው ለምንድን ነው?”
 በመጨረሻ አንድ አዛውንት ጣልቃ ገቡ፡-
“ልጆቼ፤ በእኔ ጊዜ አባቶቼ ያጫወቱኝ አንድ ጨዋታ ትዝ ብሎኝ ነው። እንዲህ እንደኛ ጦርነቱን ይገመግሙ ነበር አሉ።”
“አንድ ጦርነት ላይ ሽንፈት የሚመጣው አንድም ከዝግጅት ማነስ፣ አንድም ከሃይል እጥረት፣ አለበለዚያ ከአመራሩ ብቃት ማነስ ነው ይባላል። ጀግናው ግን “በምን ምክንያት ተሸነፋችሁ? የጠላት ወታደሮች ብዙ ነበሩ እንዴ?” ተብሎ ሲጠየቅ፤
“ብዙማ ቢሆኑ አንድ ለአንድ እንይዛቸው ነበር። አንድ ብቻውን ሆኖ ውር ውር እያለ፣ እኛኑ እርስ በርስ እያጋጨ፣ እያተረማመሰ ጉድ አደረገን እንጂ!” ብሎ መለሰ አሉ።
***
አቶ መንግስቱ ለማ የተባሉት የሀገራችን ጸሐፌ ተውኔትና ገጣሚ በ”ባለ ካባና ባለ ዳባ” ቴአትራቸው ውስጥ፡-
“ቀማኛን መቀማት፣ ከሌባ መስረቅ
ለማቅለል ከሆነ፣ የድሆችን ጭንቅ፤
በኔ ቤት ጽድቅ ነው፤ አንድ ሰው ይሙት
አንድ መቶ ሺ ሰው፣ ኪኖር በምጽዋት” ይሉናል። ዞሮ ዞሮ የአንድ ሰው ዲክታተርነት ለማንኛችንም አይበጀንም ለማለት ነው! አገራችን ኢትዮጵያ ደግሞ አምባገነን መሪ ወይም መሪዎች አጥታ አታውቅም። መሪዎች በተለዋወጡ መጠን የቅርጽ እንጂ የይዘት ለውጥ አለማየታችን፣ የሁልጊዜና ያፈጠጠ ዕውነት ነው! በአንድ ጀንበር ለውጥ ለማምጣት አቅሙ የለንም። ፍቃደኝነቱንም ለማዳበር ዝግጁነቱ የለንም። ከሁሉም በላይ ደግሞ ወጣቱ ትውልድ ላይ ብዙ አልሰራንም! ያለነዚህ ቁልፍ አጀንዳዎች ወደፊት እንጓዝ ማለት… “ሒማሊያ ተራራን በሁለት ቆራጣ እግር መውጣት” የሚባለውን የህንዶች ተረት ሥራ ላይ እናውለው፤ የማለት ያህል ነው። ለውጥ አዳጊ እንጂ በአንድ ጊዜ የሚፈጠር ጉዳይ አይደለም።
በለውጥ ውስጥ የምሁራን ሚና የላቀ ነው። ለውጥ የብዙኃንን ተሳትፎ የማታ የማታ ይጠይቅ እንጂ በጥቂት ግንባር- ቀደም የፖለቲካ ሰዎች መነሳሳቱ ያለ፣ የነበረና ወደፊትም የሚኖር ነው። ጥቂቶቹ አብሪዎች፣ ህሩያን ሕዳጣን ይሁኑ እንጂ ብዙኃኑን ይታደጋሉ። “ፀሐይ የሚያሞቀው የፒራሚዱን አናት ነው” ይባላል። The tip of the ice-berg melts first እንደሚሉት መሆኑ ነው!
ሌላው ዋንኛ የለውጥ አንኳር የኢኮኖሚው ክፍል (Sector) ነው። አብዛኛውን ጊዜ ፖለቲካው የኢኮኖሚው የተከማቸ ነጸብራቅ መሆኑን እንረሳለን። ሆኖም ኢኮኖሚ የአንድ ሀገር ሐብለ-ሠረሠር ነው። የኢኮኖሚውን ችግር የማይነካ (የማያንጸባርቅ) ፖለቲካ የይስሙላ ነው! ሥሩ ሳይኖር ዛፉ የለምና! ስለዚህ ለኢኮኖሚያችን  ብርቱ ትኩረት እንስጥ!
ፖለቲካውንና ኢኮኖሚውን ካነሳን ዘንድ የሚቀረን የማህበራዊ ኑሮ ማሠሪያ የሆነው ባህላችን ነው። እንደ ኢትዮጵያ ባሉ የብዙ ብሔር ብሔረሰብ አገራት፣ ባህልና ታሪክ እጅግ ከባድና ቁልፍ ሚና አላቸው። ስለዚህም ጥልቅ ጥናት ምርምርና ስርዓትን ይሻሉ። ከትውልድ ትውልድ የሚደረገው ቅብብሎሽም በትምህርትና በዕውቀት መሳሪያነት አገርን የማሳደግና የመለወጥ ሥር-ነቀል ሽግግርን ሊያስከትል የሚችለው በዚህ ጥበብ ነው። ለዚህ ደግሞ የኪነ-ጥበብ አስተዋጽኦ እጅግ ሰፊ ሥፍራ አለው። ንቃተ ህሊናን የማትባትን ተግባር ሥራዬ ብሎ በያዘ  መንግስት ቀዳሚ ትኩረት የሚሰጠው ሊሆን ይገባል።
የመንግስት ራሱን ማጽዳት (Purging oneself) የሁልጊዜ እንቅስቃሴ መሆን አለበት። መዛግን፣ መሸርሸርን፣ ንትበትን፣ መበስበስን መከላከል የሚቻለው ሳያቋርጡ ተሐድሶን በማድረግ ነው። ይህን ካላደረግን ንቅዘት ይከተላል። ይህንን ንቅዘት ለመቆጣጠርና በጊዜ ለማሸነፍ ተብሎ እንጂ “ለቁርጡ ቀንማ ሁሉም የክት አለው!” ለማለት አያቅትም።
እንደተለመደው “ትምህርታችንን ይግለጥልን” ብለን እናሳርግ!

    5ኛው የኢትዮጵያ ሪል እስቴትና መኖሪያ ቤት  ኤክስፖ በመጪው ታህሳስ 8 እና 9 ቀን 2015 ዓ.ም በአዲስ አበባ ስካይላይት ሆቴል እንደሚካሄድ ተገለፀ፡፡
በዚህ ኤክስፖ መጠነ-ሰፊ የሪል እስቴት መኖሪያ ቤቶች፣ አገልግሎቶችና አልሚዎች ለቤት ፈላጊዎች የሚቀርቡበት ነው  ተብሏል፡፡
ኤክስፖው ባለፉት ዓመታት በኢትዮጵያ ከተሞች፤ በተለይም በአዲስ አበባ፣ የመኖሪያ ቤቶች ፍላጎት በከፍተኛ ደረጃ ባደገበት ወቅት የሚካሄድ መሆኑም ተጠቁሟል።
የዓለም ባንክ መረጃ እንደሚያሳየው፤ በመጪዎቹ ዓመታት የኢትዮጵያ የከተማ መሬትና የከተማ ህዝብ ብዛት በከፍተኛ ደረጃ እንደሚያድግ የሚጠበቅ ሲሆን ይህም ተጨማሪ የመኖሪያ ቤት ፍላጎት ይዞ ይመጣል ተብሏል።
“251 ኮሙኒኬሽንና ማርኬቲንግ” ፤ እያደገ ለመጣው የሪል እስቴት መኖሪያ ቤቶች ፍላጎት ምላሽ ለመስጠት እንዲሁም ቤት አልሚዎችና ሸማቾች የሚገናኙበት መድረክ ለመፍጠር ባለፉት ዓመታት አራት ስኬታማ ኤክስፖዎችን ማዘጋጀቱን አስታውሶ፤ በእነዚህም መድረኮች ለመጀመሪያ ጊዜ በሺዎች የሚቆጠሩ ጎብኚዎችና ግንባር ቀደም የአገር ውስጥና ዓለማቀፍ  አልሚዎች በአንድ ጣራ ሥር መገናኘት መቻላቸውን አመልክቷል።
 የዘንድሮው 5ኛው የሪል እስቴትና መኖሪያ ቤት አልሚዎች ኤክስፖ ታህሳስ 8 ቀን 2015 ዓ.ም የመንግስት ባለሥልጣናት፣ ተጋባዥ እንግዶችና የሚዲያ አባላት በተገኙበት በስካይላይት ሆቴል በይፋ እንደሚከፈትም ታውቋል፡፡
ላለፉት አስርት ዓመታት ትላልቅ ዓለማቀፍ ኹነቶችን በማዘጋጀት የዳበረ ልምድ ያካበተው “251 ኮሙኒኬሽንና ማርኬቲንግ”፤ 5ኛውን የሪል እስቴትና መኖሪያ ቤት አልሚዎች ኤክስፖ ለማካሄድ ዝግጅቱን ማጠናቀቁን ለዝግጅት ክፍላችን በላከው መግለጫ አስታውቋል፡፡



     በ20 ዓመታት ውስጥ ባለ ብዙ ፋሲሊቲ ሜትሮፖሊስ (ከተማ) ለማቋቋም አቅዷል

        ብሬክስሩ ትሬዲንግ አ.ማ. ዓመታዊ የሽያጭ ዕቅዱን በ65 በመቶ በማሳካት 65 ሚሊዮን ብር ገቢ ማግኘቱን አስታወቀ፡፡
ባለፈው ረቡዕ በሸራተን አዲስ በተካሄደው ሦስተኛው መደበኛ የባለአክሲዮኖች ስብሰባ ላይ የዳይሬክተሮች ቦርድ ሰብሳቢ የሆኑት አቶ ነፃነት ዘነበ እንደተናገሩት፤ የ2014 በጀት ዓመት የሽያጭ መጠን 65 ሚሊዮን ብር ደርሷል።
ጠቅላላ ጉባኤው በ2014 የበጀት ዓመት 100 ሚሊዮን ብር ገቢ  ዕቅድ ቢያስቀምጥም፣ ድርጅቱ የዕቅዱን 65 በመቶ በማሳካት፣  65 ሚሊዮን ብር ገቢ ማግኘቱን የቦርድ ሰብሳቢው አስታውቀዋል።
“የባለአክሲዮኖች ድርሻ በሽያጭ ካገኘነው ገቢ 50 በመቶው ነው” ሲሉም ገልፀዋል፡፡ በ2014 የበጀት ዓመት የኩባንያውን ንግድ ለማስፋፋት የተነደፈውን ዕቅድ አፈጻጸም ላይ በስኬት መድረሱንም አቶ ነፃነት ተናግረዋል።
“ዓለም አቀፍ ደረጃቸውን የጠበቁ ቅርንጫፍ ጽህፈት ቤቶችን ለመክፈት ባቀድነው መሰረት በአዲስ አበባና አዳማ ከተማ ሁለት ቅርንጫፎችን መክፈት ችለናል” ብለዋል፤አቶ አቶ ነፃነት። “በደቡብ ሱዳን፣ ናይጄሪያ፣ ኬንያና ካሜሩን ቢሮ ለመክፈት የምናደርገውን ጥረት እውን ለማድረግ የሚያስችል በጀት መድበናል። በተጨማሪም፣ መንገዶችን ለማመቻቸት የሚረዱ ሃሳቦችን ከተወሰኑ ግለሰቦች ጋር በመለዋወጥ ስምምነት ላይ ደርሰናል። ብሬክስሩ ከዚህም ባሻገር “ጆብ ክርኤሽን” ከተባለ የኬንያ ኩባንያና ከደቡብ አፍሪካው ስታንዳርድ ባንክ ጋር በጋራ ለመስራት የሚያስችል የጋራ ስምምነት ተፈራርሟል” ሲሉም ገልጸዋል፤ሰብሳቢው፡፡
ጠቅላላ የባለአክሲዮኖቹ ጉባኤ ተወያይቶ የኦዲትና አጠቃላይ ሪፖርቶችን እንደሚያጸድቅ የተገለጸ ሲሆን፤ የ2015 በጀት ዓመት የበጀት ድልድልና የኩባንያው የስራ ዕቅድም ለውይይት ቀርቦ እንደሚጸድቅ በበዓሉ ላይ ከተሰራጨው መግለጫ ለመረዳት ተችሏል።
ብሬክስሩ ትሬዲንግ፤ አርቆ አስተዋይ፣ ጤናማና ባለፀጋ ትውልድ የመገንባት ራዕይ ያለውና “ቅን” በተሰኘ ቡድን በ2019 ዓ.ም የተመሰረተ የንግድ ኩባንያ ሲሆን፤ ባለፉት ሁለት ዓመታት ለንግድ ድርጅቶችና ግለሰቦች የተሻሉ አዳዲስ ፈጣሪዎች እንዲሆኑ፣ የየራሳቸውን ንግድ በዲሲፕሊን እንዲያከናውኑና ከሌሎች ጋር ውጤታማ ትብብር እንዲፈጥሩ የማማከርና የስልጠና አገልግሎቶችን መስጠቱ ተጠቁሟል፡፡
ብሬክስሩ ትሬዲንግ፤ በ20 ዓመታት ጊዜ ውስጥ ኩባንያዎችን፣ ሆስፒታሎችን፣ የሥልጠና ማዕከሎችን፣ የስብሰባ ማዕከላትን፣ ዩኒቨርሲቲዎችን፣ ሪል እስቴትን፣ ቢሮዎችን፣ የኢንዱስትሪ ፓርኮችን፣ ጂምናዚየሞችን፣ ሙዚየሞችንና ሌሎች ተመሳሳይ አገልግሎት መስጫ ተቋማትን የሚያቅፍ ባለብዙ ፋሲሊቲ ሜትሮፖሊስ (ከተማ) ለማቋቋም ማቀዱ ታውቋል።
           

      25 ሺ ገደማ ኢትዮጵያውን በኳታር ይኖራሉ

       ግሩም ሰይፉ ጋዜጠኛ ነው። አዲስ አድማስ ለተሰኘው ጋዜጣ ስፖርታዊና ማኅበራዊ ጉዳዮችን በመፃፍ ይታወቃል። ግሩም የኳታር የዓለም ዋንጫ ዝግጅትን ለመታደም ወደ ዶሃ ያቀናው ከመክፈቻው ጥቂት ቀናት ቀድሞ ነው።
ዶሃ ከአዲስ አበባ 2200 ኪሎ ሜትር ገደማ ርቀት ላይ ትገኛለች። የኢትዮጵያ አየር መንገድ ኳታር ኤርዌይስ በየቀኑ መንገደኞችን ያመላልሳሉ።
ግሩም፤ ነፋሻማዋን አዲስ አበባ ለቆ ወደ ዶሃ ሲያመራ የጠበቀው የግንቦት ሃሩር ነው። ነገር ግን ይህ ወቅት ለኳታሮች ቀዝቃዛው ወር ነው።
“ዶሃ የቀትር ፀሐይ የሚባል የለም” ይላል። ምክንያቱም ቀኑን ሙሉ የዶሃን አሸዋማ መሬት የሚቀጠቅጠው ፀሐይ ሃሩር ነው።
ኳታር፤ በሜትሮሎጂ ዘገባ አገላለፅ፤ “በአብዛኛው ፀሐያማ” ናት። በአብዛኛው ከማለት ከንጋት እስከ ምሽት ማለት ሳይቀል አይቀርም። አሁን ባለው የአገሪቱ የአየር ሁኔታ ዝቅተኛው የሚባለው 23 ድግሪ ሴንትግሪድ የሚጀምረው ሌሊት 10 ሰዓት ገደማ ነው።
ዎርልድ ፖፑሌሽን ሪቪው የተሰኘው ድረ-ገፅ፣ የኳታር ሕዝብ ብዛት በዚህ ዓመት 2.7 ሚሊዮን ይገመታል ይላል።
ከእነዚህ መካከል ካታሪ የሚባሉት አረቦች 15 በመቶውን ይይዛሉ። ሕንዳዊያን፣ ፊሊፒናውያን እንዲሁም ሌሎች የእስያ አገራት ዜጎች ኑሯቸውን በኳታር ይመራሉ።
ከዚህ ባሻገር በርካታ ኢትዮጵያዊያን፣ ኤርትራዊያንና ኬንያዊያን በዋና ከተማዋ ዶሃ እንዲሁም በአር ራያን ይገኛሉ።
በነዳጅ ሃብት የበለፀገችው ኳታር፤ እነሆ በአረቡ የዓለም ሲዘጋጅ የመጀመሪያው የሆነውን የዓለም ዋንጫ በማስተናገድ ላይ ትገኛለች።
ቶለመ
“ኢትዮጵያዊያን የሥራ ሰዎች ናቸው ይባላሉ”
ግሩም፤ ካሜሩን ከሰርቢያ የሚያደርጉትን የቀን 7 ሰዓት የምድብ ጨዋታ ታድሞ ለመዘገብ እየተጓዘ ሳለ ነው በስልክ ያገኘነው። በየገባህበት ሥፍራ ሁሉ የአየር ማጤዣ ተገጥሟል የሚለው ግሩም፣ ይህ ቴክኖሎጂ ባይኖር ኖሮ ኳታር ለኑሮ ከባድ ትሆን እንደነበር ይናገራል።
“አሁን ለምሳሌ በአገሩ ሰዓት አቆጣጠር 5 ሰዓት ከምናምን ነው። እኛ አገር ግንቦት ወር ላይ ያለው የሚያማርረው ሙቀት ነው አሁን እዚህ ያለው።”
ግሩም የኳታር ነዋሪዎችን ስለ አየር ሁኔታው ሲጠይቃቸው፤ “በብርድ ወቅት መጣህ” በሚል ዓይን እያዩት፤ “ኧረ እንዲያውም ይሄ እኮ ቀዝቃዛው ጊዜ ነው” ይሉታል።
ኳታር፤ ለዚህ ነው ይህንን ወቅት ለዓለም ዋንጫ የመረጠችው እንጂ ለወትሮው የዓለም ዋንጫ በሰኔ ነበር  የሚዘጋጀው።
ከፋርስ ባሕረ ሰላጤ የሚነሳው ነፋስ፣ የኳታር ምሽትን ቀዝቀዝ አድርጎታል።
ኳታር፤ ይህን የዓለም ዋንጫ ስታዘጋጅ ከምዕራቡ ዓለም ከፍተኛ ተቃውሞ ደርሶባት ነበር። አገሪቱ የሰብዓዊ መብት አይከበርባትም፣ ስታድየሞቹ ሲታነፁ በርካታ የጉልበት ሠራተኞች ሞተዋል፣ የአየር ሁኔታው ምቹ አይደለም. . . ብቻ ብዙ ነቀፋ አስተናግዳለች።
ነገር ግን ጋዜጠኛ ግሩም፤ ይህ ነቀፋ ተጋኗል የሚል እምነት አለው። “የኳታር ዜጎች በጣም ሰላምተኞች ናቸው። እንግዳ ተቀባይነታቸውን ማየት ችያለሁ። በአረቡ ዓለም መዘጋጀቱ የአረቡ የዓለም ለእግር ኳስ ያለውን ፍቅር ለማሳየት ልዩ አጋጣሚ ነው” ይላል።
ኻሊፋ ኢንተርናሽናል ስታዲየም
እንደሱ አመለካከት፤ ዶሃ ወደፊት ልክ እንደ ዱባይ ከተለያዩ የዓለም ክፍሎች የሚመጡ ጎብኚዎች የምታስናግድ መናኸሪያ እንደምትሆን አምነት አለው።
ግሩም፤ በዶሃ በተዘዋወረባቸው ቦታዎች በርካታ ኢትዮጵያውያን ኑሮን ለማሸነፍ በተለያየ ሥራ ተሠማርተው ሲተጉ አይቷል።
“ስታዲየሞች ውስጥ በጎ ፈቃደኛ ኢትዮጵያውያንን አግኝቻለሁ። አንድ የሥነ-ጥበብ ባለሙያ ኢትዮጵያዊም ተዋውቄያለሁ። በዓለም ዋንጫው ከትላልቅ የብሮድካስት ኩባንያዎች ጋር የሚሠራ ኢትዮጵያዊም ማግኘት ችያለሁ።”
ጋዜጠኛው ግሩም እንደሚለው፤ ከ20 ሺህ በላይ ኢትዮጵያውያን ኳታር ውስጥ ይኖራሉ።
ስለአገሪቱ የተለያዩ መረጃዎችን የሚያወጣው ‘ኦንላይን ካታር’ የተሰኘው ገፅ፤ ቢያንስ 25 ሺህ ኢትዮጵያዊያን እንደሚገኙ አስፍሯል።
“በቤት ሠራተኝነት የሚሠሩ አሉ። የሚማሩ አሉ። የሕንፃ ግንባታ ባለሙያዎች፤ የታክሲ ሾፌሮች አሉ። በርካታ የኢትዮጵያ ሬስቶራንቶች ያሉበት አንድ አካባቢ አለ። አዲስ አበባ የሚል ስያሜ ያለው ፀጉር ቤት አይቻለሁ። እኔ ከጎበኘኋቸው ሬስቶራንቶች በአንዱ በርካታ ኢትዮጵያዊያን ተሰባስበው አይቻለሁ።”
“ኢትዮጵያውያን በኳታሮች ዘንድ ይከበራሉ።” የሚለው ግሩም፤ “የሥራ ሰዎች ናቸው ይባላሉ” ብሏል።
ጋዜጠኛ ግሩም ከዚህ ቀደም ወደ ደቡብ አፍሪካ እንዲሁም ሩሲያ ተጉዞ የዓለም ዋንጫን መታደም ችሏል። ነገር ግን የዶሃው በብዙ መልኩ እንደሚለይ ይገልጻል።
አንደኛው ምክንያት፤ ስታድየሞቹ የተቀራረቡ በመሆናቸው እሱና የሙያ አጋሮቹ በአንድ ቀን የተለያዩ ጨዋታዎችን መታደም መቻላቸው ነው።
ለምሳሌ በሩሲያው የዓለም ዋንጫ ከዋና ከተማዋ ሞስኮ ወደ ሶቺ ለመሄድ 72 ሰዓታትን በባቡር ተጉዞ ነበር።
ከዚህ በፊት ከተመለከታቸው የዓለም ዋንጫዎች በተለየ በምድብ ጨዋታዎች የታየው ፉክክር፣ የተመልካቾች ብዛትና የስታዲየሞቹ ልዩ ‘ዲዛይን’ ይህንን የዓለም ዋንጫ “ለየት አድርጎብኛል” ባይ ነው የአዲስ አድማሱ ግሩም ሰይፉ።

Saturday, 03 December 2022 12:30

ከሶሻል ሚዲያ በጨረፍታ


                         ልጆችን እንጂ ልጅነትን ማስቆም አይቻልም!
                            አሌክስ አብርሃም

         ወላጆች  ልጅ ሲወልዱ ድካምና ውጣውረዱን የሚችሉበት ፍቅር አብሮ ባይሰጣቸው ኖሮ … ገና በዓመታቸው ዳይፐራቸውን እያስያዙ ከቤት ያባርሯቸው ነበር፡፡ ልጅ ማሳደግ አዲስ ከዚህ በፊት ያልነበረ ሰው መስራት ሊባል ይችላል፡፡ልጅ ማሳደግ  የራስን ፍላጎት  አምሮትና ማንነት ጭምር መተው የሚጠይቅ ከባድ ኃላፊነት ነው። ያስደስታል፣ ያበሳጫል፣ አንዳንዴም ፀጉር ሊያስነጭና ሊያስለቅስ ይችላል!  ለዛም ነው ከመውለድ በፊት ደግሞ ደጋግሞ ማሰብ ወሳኝ ነው የሚባለው፡፡ እሽ አስበንም ይሁን ሳናስብ ልጅ ተወለደ ከዛስ? የዚህ ፅሁፍ ዓላማ ይሄ ነው …
አንዳንድ ወላጆች ህፃናት ልጆችን ወደቤታቸው  የመጡ ተጨማሪ ፍጥረቶች እንጅ ልክ እንደነሱ ከተወለዱበት ቀን ጀምሮ የቤቱ ባለቤት መሆናቸውን አያስቡትም፡፡ በህፃናትና ወላጆች መካከል የሚፈጠረው ‹‹ጦርነት››  ሁሉ፣ ልጆች የባለቤትነት መብታቸውን ለማስከበር የሚያደርጉት የህፃን ጥረትና ወላጆች የልጆቹን ባለቤትነት ለመንፈግ የሚያደርጉት የአዋቂ ክልከላ ውጤት ነው፡፡
ምሳሌ:-  ልጆች የፈለጉት የቤቱ ክፍል ላይ መጫወቻቸውን ማስቀመጥ (መዝረክረክ)፣ እቃዎችን መገለባበጥ፣ መንጠላጠል፣ ማቆሸሽ፣ የሚሰበር ዕቃ ካገኙ መስበር ፣እጃቸው ላይ ባገኙት እርሳስ፣  ከለር  ከሰል ሊፕስቲክ ኩል ወዘተ ያገኙት ነገር ላይ መፃፍ  መሳል ይፈልጋሉ! ወላጆች ደግሞ እነሱ የወሰኑላቸው ቦታ ላይ ብቻ እንዲጫወቱ ፣የፈቀዱላቸውን ዕቃ ብቻ እንዲነኩ ይፈልጋሉ …በዚህ ትግል መሃል ለቅሶው፣ ቁጣው፣ ማስፈራሪያው፣ ማስጠንቀቂያው ገፋ ካለም ቁንጥጫው ነጠላ ጫማው … ዓለም የማይዘግበው ጦርነት ሁሉ በየቤቱ ይኖራል! የወላጆችን ክልከላ ከልጆች ደህንነት እንዲሁም ከቤት ውበት አንፃር ለሁለት ከፍሎ ማየት ይቻላል፡፡ የሆነ ሆኖ ክልከላ የት ድረስ?
በተለይም በአበሻ ወላጆች ዘንድ በስፋት የተለመደ አንድ ጉዳይ አለ …ይሉኝታ ! እንግዳ ወደ ቤት ከመጣ ልጆች ቤት እንዳያዝረከርኩ፣ እንዳይንቀዠቀዡ ከባድ ማዕቀብ ነው የሚጣልባቸው! ይህም ከጨዋነት ይቆጠራል፡፡ እንግዳ የቤቱን ውበት፣ የልጆቹን ባህሪ መበላሸት ታዝቦን እንዳይሄድ እንፈራለን! አንዳንድ እንግዳ እንደውም አስተያየት ሁሉ ይሰጣል ‹‹አይ እነዚህን ልጆች አቅበጣችኋቸዋል፤ አሁን የእንትና ልጅ  ገና እናቱ በዓይኗ ስትገለምጠው ነው እጅ በደረት አርጎ የሚቀመጠው....!›› ስለዚህ በእንግዶች ፊት ክብራችን ከፍ እንዲል፣ ከእንትናም እናት ላለማነስ፣ ልጆቹን በምንም ይሁን በምን ለጊዜው የእስር ቤት አይነት ክልከላ እንጥልባቸዋለን! የልጆች ተፈጥሮ ደግሞ አሳሽነት  ነው፣ መፈለግ ነው መንካት ነው፣ መሞከር ነው! በደመነፍስ መንቀሳቀስ ነው  ማዝረክረክ ነው …የፈለጉትን በፈለጉበት ጊዜ እንጅ በኋላ እንግዳ ሲሄድ የሚል ነገር አይገባቸውም! ይሄን ተፈጥሯቸውን ወላጆች ብቻ ሳይሆኑ ራሳቸውም መቋቋም አይችሉም! ልጆች ልጅነትን አይቋቋሙም!
እንግዳም ባይኖር ብዙ  ወላጆች  ቤታቸውን የሚያደራጁበት መንገድ ፈፅሞ ለልጆች የማይመች ነው! (የቤት ችግር እንዳለ ሆኖ) ገና ሲያረግዙ ለአራስ ጥየቃ የሚመጣውን ወዳጅ ዘመድ ታሳቢ በማድረግ፣ አልያም ራሳቸውን ስለሚያስደስታቸው፣ ወይም የሆነ ሰው ቤት ስላዩት  ቆንጆ የቲቪ ማስቀመጫ ጠርዙ ከመሳሉ የተነሳ ዶሮ የሚያርድ … ጫፍና ጫፉ እንደጦር የሾለ በውድ  ዋጋ ይገዛሉ፣ ትልቅ ፍላት ስክሪን ቲቪ ያስቀምጡበታል፣ ልጆች ቶሎ ያድጋሉ፣ ብዙዎቻችን እቃ የመቀየር አቅሙም ባህሉም የለንምና ቦታ እንኳን ሳይቀያየር ይደርሳሉ! በቀላሉ ስለሚደርሱበት ቲቪ ማስቀመጫው ላይ መንጠላጠል፣ ቲቪውን መንካት አስፈላጊ ከሆነም ባገኙት እቃ መኮርኮም ይፈልጋሉ!  ከፈለጉ ደግሞ ያደርጉታል! ወላጅ የዕቃዎቹን ውድነት ከልጆቹ ነፃነት ያስቀድማል! በውድ ዋጋ የገዛው ሶፋ ላይ ሽንታቸውን ሊሸኑ ምግብ ሊያንጠባጥቡ …ወተት ሊደፉ ይችላሉ …ወላጅ በብስጭት ድፍት ሊል ምንም አይቀረውም! ችግሩ ከየት መጣ?
ቤታችሁ ውስጥ  ከጥግ እስከ ጥግ ኤንትሬ ከነተሳቢው የሚያክል ሶፋ ትገጠግጣላችሁ፣ በዛ በኩል ብሔራዊ ሙዚየም የሚቀናበት ቡፌ በብርጭቆና ምናምን አጭቃችሁ  ታቆማላችሁ... አየር አያሳልፍም እንኳን ሰው! …በዛ ላይ የአንዳንዶቻችን  የቀለም ምርጫ እንኳን ልጆችን አዋቂ በድብርት የሚገድል ነው! ከዛ የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ በልጆቻችሁ ላይ ታውጁና ሚስት ወጥ ማማሳያ፣ ባል ቀበቶ ይዛችሁ ትቆማላችሁ! የቤተሰብ “ኮማንድ ፖስት”!
ልጆች ላይ መጮህ፣ መምታት፣ ማስፈራራትን እንደ መከላከያ ይወሰዳል! የዚህ ሁሉ ችግር መነሻው ገና ከጅምሩ ልጆችን የቤቱ ባለቤት ሳይሆን ተጨማሪ እንደ ወላጆቻቸው ፍላጎት ብቻ የታዘዙትን እያደረጉ የሚኖሩ ፍጥረቶች አድርጎ ማሰብ ነው፡፡ ልክ ባል ወይም ሚስት ለእነሱ የሚመቻቸውን የእቃ አቀማመጥ እንደሚወስኑ ሁሉ ለልጆቹንም ታሳቢ ያደረገ  የእቃ፣ የከለር የአቀማመጥ ሁኔታዎችን አቅም በሚፈቅደው ማመቻቸት ግድ ይላል! ምክንያቱም …ልጆችን ማስቆም ይቻል ይሆናል፣ ልጅነትን ማስቆም ግን አይቻልም:: …ልጆች ፊታችሁ የቆሙ ትንንሽ ፍጥረቶች ሲሆኑ ልጅነት እነዚህን ትንሽ ፍጥረቶች ጦር ሰራዊት የሚያደርግ ውስጣዊ ባህሪ ነው! ዋናው ነጥብ  (እንግዶች ሌላ እንግዳ ሆነው የሚሄዱበት ብዙ ቤት አላቸው…ልጆች ግን ልጅ ሆነው መኖር የሚችሉበት ብቸኛ ቤት ቤታቸው ብቻ ነው!)  ያዝረክርኩ፣ ግን እንዴት እንደሚያስተካክሉ ሳትታክቱ አስተምሯቸው፣ ልጆች  ዕቃዎቻችሁን እንዳያበላሹ ከምትጠነቀቁት በላይ ዕቃዎች ልጆቻችሁን እንዳይጎዱ ቀድማችሁ አስቡ ተጠንቀቁ! አመቻቹ! ሶፋ ያረጃል ይጣላል፣ ቲቪ ነገ ከጥቅም ውጭ ይሆናል፤ ልጆች ግን በምንም የማይተኩ  አስቸጋሪ፣ ‹ስማርት›  እና  ውብ ፍጥረቶች ናቸው!  
ዛሬ ቀላል የሚመስላችሁ የልጆች ጨዋታ፣ ነገሮችን ለማወቅ መጓጓት፣  የነገ ማንነታቸው ላይ ቀላል የማይባል አስተዋፅኦ አለው! መሳቢያችሁን ከፍቶ እንዳያይ፣ ቡፊያችሁን ከፍቶ የሸክላ ሰሐንና ብርጭቆ እንዳይሰብር በቁንጥጫና በጩኸት፣ በነጠላ ጫማና ቁንጥጫ እያሸማቀቃችሁ  ያሳደጋችሁትን ልጅ፤ ‹‹ልጄ ሲያድግ ናሳ ነው የሚሰራው፣ ጨረቃን ነው  የሚያስሰው…›› ትላላችሁ … ልጆች ማሰስን የሚጀምሩት ከጨረቃ አይደለም፤  ከቤት ነው! ዓለምም ህዋም ለልጆች ቤታቸው ነው፡፡ አዲስ ነገር መሞከርን የሚፈራ፣ ስህተትን የሚፈራ ይሄንና ያን ብነካ ጩኸትና ቅጣት ይከተለኛል በሚል ተሸማቆ ያደገ ህፃን፣ መፈለግ፣ ማሰስ፣ መሞከር ሳይሆን መደበቅ ነው የሚቀናው፡፡ ለዛ ነው  አብዛኞቻችን  ድብቆች ደንጋጭና ግልፅነት የሚያስፈራን፣ አዲስ ነገር ‹ነርቨስ› የሚያደርገን  ሰዎች የሆነው! ሩቅ ሳትሄዱ አስተዳደጋችሁን ዙሩና አስታውሱ! አስተዳደግ!
ሳጠቃልለው (ጨዋታ ለልጆች ቀልድ አይደለም፣ ቤታችሁ መጥቶ ለሚሄድ እንግዳ ሳይሆን፣ ለልጆቻችሁ እንዲመች አድርጋችሁ አመቻቹ! ቤታችሁ  የልጆቻችሁ ዓለም ነው! ዓለማቸውን ነገ ለማያስታውሳችሁ እንግዳ ይሁን ጎረቤት አትቀሟቸው!)  ልጆች ያዝረከረኩትን ቤት ማየት የማይፈልግ እንግዳ ፣እዛ ፓርክ፣ ቤተ መንግስት፣ ሙዚየም ምናምን ሂዶ ይጎብኝ! አንዴ ልድገመው …ቤታችሁን ንፁህ ግን ልጆች  እንዳሻቸው የሚያዝረከርኩት ይሆን ዘንድ መልካም ፈቃዳችሁ ይሁን! እናንተም እንግዳ ሆናችሁ ሰዎች ቤት ስትሄዱ ከወላጆቹ የበለጠ ለልጆች ምቹ እና ቀላል ለመሆን ሞክሩ …በሰው ዓለም አትኮፈሱ!


___________________________________________________
=================================================



                  ስለ “ሰፈራ ቅኝ አገዛዝ” (Settler Colonialism) ማን ምን አለ?
                     ጌታሁን ሔራሞ


        የሀገራችንን የኋላ ታሪክ በተመለከተ ስለ “ሰፈራ ቅኝ አገዛዝ” የሚቃረኑ እሳቤዎች ከዚህኛውም ከዚያኛውም ጎራ ሲሰነዘር እንሰማለን። ለምሣሌ ዶ/ር ነጋሶ ጊዳዳ እና ፕሮፈሰር አሰፋ ጃለታ፡፡ (የምኒልክን ወደ ደቡብ አቅጣጫ መዝመትን ከ”ሰፈራ ቅኝ አገዛዝ” አገናኝተው ይተነትናሉ። በተቃራኒው ፕሮፈሰር መሳይ ከበደ፤ (በ”Survival and Modernization” መፅሐፋቸው) እና ዶ/ር ሀብታሙ መንግሥቴ ተገኘ (የ”በራራ-ቀዳሚት አዲስ አበባ” መፅሐፍ ደራሲ) የምኒልክ ዘመቻ በ”ሰፈራ ቅኝ አገዛዝ”ነት ከተፈረጀ የኦሮሞው የሞገሳ፣ የገዳ እና የፍልሰት ታሪኮችም የ”ሰፈራ ቅኝ አገዛዝ” ይዘቶችን እንዳቀፉ ይሞግታሉ። በተለይም ሀብታሙ መንግስቴ በመፅሐፋቸው፤ (በራራ-ቀዳሚት አዲስ አበባ) ምዕራፍ ሰባት “የሰፈራ ቅኝ ግዛት፣ የባህል ድምሰሳና የዘር መሳሳት በዓለም ታሪክና በኢትዮጵያ” በሚለው ንዑስ ርዕስ ሥር ስለ “ሰፈራ ቅኝ አገዛዝ” ያነሱት፣ እነ ፕሮፈሰር አሰፋ ጃለታ ከሚያነሱት በተቃራኒው ነው።
በርዕሰ ጉዳዩ ላይ ሌሎች የሀገር ውስጥም የውጭም ፀሐፍት ብዙ ብለዋል። በእኔ ዕይታ በሁለቱም ጎራ ያሉ ዕሳቤዎች ለውይይት መቅረብ አለባቸው የሚል እምነቱ አለኝ። ምክንያቱም በአካዳሚክም ሆነ በፖለቲካ ሊሂቃን የሚነገሩ ሐቲቶች ወደ ሕዝቡ ሲደርሱ፣ ትርጉማቸው እየተዛባ፣ ግጭቶችን የመቀስቀስ ዕምቅ አቅም አላቸው። እይታዎቹ ታች ወርደው ወደ ጠብ-ጫሪነት ከመቀየራቸው በፊት፣ (ተቀይረዋልም) ሚዛናዊነትን በተላበሰ መልኩ መነጋገር ወደ መፍትሔው አቅጣጫ ይወስደናል የሚል እምነቱ አለኝ።
ስለዚህም በቅርቡ “ስለ ‘ሰፈራ ቅኝ አገዛዝ’ ማን ምን ብሎ ነበር?” በሚል ርዕስ፣ ከፅንሰ ሐሳቡም በመነሳት በሁለቱም ጎራዎች የተንፀባረቁ ሐሳቦችን ላስቃኛችሁ እሞክራለሁ። በነገራችን ላይ የ”ሰፈራ ቅኝ አገዛዝ” ፅንሰ ሐሳብ ከመደበኛው ቅኝ አገዛዝ ፅንሰ ሐሳብ እንደሚለይ ታምኖበት፣ በጥልቀት ጥናት መደረግ የጀመረው ካለፉት ሁለት አሥርት ዓመታት ወዲህ ነው።

=========================================================

                     ሙሰኞች፤ ”60 ለመንግስት፣ 40 ለእኛ” እያሉ ነው
                        ሙሼ ሰሙ


        ሙስናና ሙሰኞች የመንግስትን መዋቅር መሳ ለመሳ ገጥመው፣ የራሳቸውን የአሰራር ስርዓት ዘርግተውና “ኮሚሽን” አደላድለው፣ ኪሳቸውን እያደለቡና ሀገር እያፈረሱ እንደሆነ በስፋት እየተነገረ ነው።
መፈክራቸውም  60 ለመንግስት፣ 40 ለእኛ (ሙሰኞች) እንደሆነም እየሰማን ነው። ሙስና ስጋ ለብሶ ነፍስ ገዝቶ በሕዝብና በመንግስት መሃል  በኩራት መንጎማለሉ ሳያንሰው፣ የሚያከብረውና የሚፈራው ሕግ፣ የሚያሸማቅቀውና የሚያፍረው የሞራል መዳድል እንደጠፋም እየተገለጸ ነው።
ይህ እንግዲህ ቱባ ቱባ ሙሰኞች ሲዘከሩ የምንሰማው ወቅታዊ ትርክት ነው። በሙስና ከተጨማለቁትና በሕገ ወጥ መንገድ ሀብት ጠግበው ከሚተፉት ባለሃብቶችና አስፈጻሚ የመንግስት ጋሻ ጃግሬዎች የጥጋብና የፈንጠዝያ ዓለም ወረድ ሲባል፣ በአስተዳደራዊ በደልና በአገልግሎት እጦት በየእለቱ እየተንከራተቱና ደም እንባ እያለቀሱ ያሉ ዜጎች መኖራቸው ፈጽሞ የተረሳ ይመስላል።
ከጥቂት ዓመታት በፊት ሰዓት የማይፈጅ አንድ ተራ አስተዳደራዊ ጉዳይ ለማስፈጸምና አገልግሎት ለማግኘት ከቢሮ ቢሮ፣ ከአስፈጻሚ  አስፈጻሚ መንከራተት፣ መረጃህ የለም፣ ሰነድህ ጠፍቷል፣ ነገ ተመለስ፣ አይመለከተኝም፣ የራስ ጉዳይ፣ ምን ታመጣለህ መባል፣ መንጓጠጥ፣ መገላመጥና የፈለክበት ሂድና ክሰስ  መባል የእለት ከእለት ኑሯችን ሆኗል።
ሙስና በስልጣን ከመባለግና ስልጣንን ተገን አድርጎ ያልተገባ ጥቅም ከማግኘት ባሻገር ሰፊ የበደልና የግፍ ጉሮኖ መሆኑም ተዘንግቷል። የአሰራር ብልሹነት፣ አስተዳደራዊ በደል፣ ተገልጋይ ማጉላላትና ማንገላታት፣ በስራ ሰዓት አለመገኘት፣ የስራ መደብን ጥሎ መጥፋት የመሳሰሉት ኑሮህን እንድታማርርና እራስህንና ሀገርህን እንድትጠላ የሚያደርጉህ ግፎችና በደሎች የሙስና ዓይነተኛ መገለጫ መሆናቸው ከመዝገብ ተፍቋል። አስዳደራዊ በደሎችና ግፎች አብዛኛውን ሕዝብ የሚመለከቱና ከቱባ ሙሰኞችና አቀናባሪዎቻቸው ዘረፋ በላይ እጅግ የላቁ ጉዳት አድራሽና ትኩረት የሚሹ ጉዳዮች መሆናቸው ተረስቷል ።
የሙስና ትግሉ ግብ ለቱባ ሙሰኞች አዳዲስ ኮሚቴ ከማቋቋምና መረጃ ከማሰብሰብ ባሻገር፣ ሰፋ አድርጎ ሊፈትሸውና ትኩረት ሊሰጠው የሚገባው ጉዳይ  አስቻይ (Enabling) ሁኔታዎቹ መታገል መሆኑ፣ ሰሚ ጆሮ ያጣ ጩኽት ነው።
ትኩረትና ትግል የሚሹ አስቻይ ( Enabling) ሁኔታዎች በጥቂቱ እንቃኝ፡
አንደኛው ለሙስና አስቻይ ሁኔታ ሳይሰሩ፣ ሳይለፉና ሳይደክሙ በዘረፋና በንጥቂያ መክበር የማያስጠይቅ መብት መሆኑ ነው። ካለፉት ጥቂት ዓመታት ወዲህ በከፍተኛ ደረጃ ስር እየሰደደና ባህል እየሆነ የመጣው ሳይሰሩ፣ ሳይለፉና ሳይደክሙ ሆኖና መስሎ በመገኘት ብቻ  ያዩትንና የሰሙትን ሀገራዊና ግለሰባዊ ሀብት፣ የኔ ነው በማለት መቀራመትን የሚያበረታታ አስተዳደራዊና ስነ ልቦናዊ አስቻይ ሁኔታ ስር እንዲሰድ መፈቀዱ ነው ።   
ሁለተኛው አስቻይ ሁኔታ ጦርነቱ ነው። ጦርነቱን ተከትሎ በተፈጠረው ውጥረትና ቀውስ ምክንያት የመንግስት የትኩረት አቅጣጫ መዛበት፣  ጥቂት ስርዓት አልበኞች አጋጣሚውን ተጠቅመው በዘረፋና በሙስ እንዲሰማሩ፣ እንደፈለጉ እንዲፈነጩና እንዲከብሩ እድል መፍጠሩ ነው።
ሶስተኛው አስቻይ ሁኔታ የክልከላ፣ የእገዳ፣ የስርዓት መፋለስና  የአሰራር መጨማለቅ የማን አለብኝነትና የቸልተኝነት ስር መስደድ ነው። ቤት መሸጥ፣ መሬት መሸጥ፣ መታወቂያና መንጃ ፈቃድ ማደስና ማውጣት፣ ንብረት ማዛወር የመሳሰሉት መሰረታዊ መብቶች መታገዳቸው በሕገ ወጥ መንገድ መታወቂያ በገፍ መታደሉ ወዘተ መገለጫዎቹ ናቸው። ይህ ተግባር ዜጎች መብታቸውን ለማስከበር አቋራጭ እንዲፈልጉና መብታቸውን በጉቦ እንዲገዙ አድርጓል።
አራተኛው አስቻይ ሁኔታ :- የስልጣን ምንጭ ችሎታና ብቃት, ከመሆን ይልቅ ታማኝነት መሆኑ ነው። በታማኝነት የተገኘ ስልጣን አስተማማኝ አይደለም። የተሻለ ታማኝ እስኪመጣ ድረስ ካልሆነ  በስተቀረ የስራ ዋስትናና በስልጣን ላይ መቆየት አስተማማኝ አይደለም። ለዚህ ደግሞ በተገኘው አጋጣሚ ሁላ በሙስና ተዘፍቆ፣ ዘርፎና አተራምሶ ነገን አስተማማኝ ማድረግ የአሽከሮች ምንዳ መሆኑ ነው።
የሙስና ትግል የትልልቆቹ አሳዎች ጉዳይ ብቻ ሳይሆን ሕዝብ የሚያስመርሩና ደም የሚያስለቅሱ የትንንሾቹም ሙሰኞች ጉዳይ መሆን አለበት። የግል ዘርፉ፣ የትምህርትና የሃይማኖት ተቋማት የተዘፈቁበት የሙስና ስፋትና ጥልቀት እንደ ሀገር የሰመጥንበትን የመበስበሰሰ ደረጃ የሚጠቁም ነው። የሙስና ትግሉ መጀመር ያለበት የትናንት ሙሰኞችን በማሳደድ ላይጨብቻ አተኩሮ ሳይሆን የነገ ሙሰኞችን ከወዲሁ ለመመከት በሚረዳ መልክ ለሙስናና ዘረፋ  መንስኤ የሆነ ስነ ልቦናዊ፣ ፖለቲካዊና አስተዳደራዊ አስቻይ ሁኔታዎችን በመታገል ጭምር መሆን አለበት።


 የአርጀንቲናው የስፖርት ሊቅ ሊቺያኖ ወርኒኪ፤ ከኳታር  የዓለም ዋንጫ 2022 መክፈቺያ ጥቂት ቀደም ብሎ ባሳተመው “The Most Incredible World Cup Stories “ የተሰኘ መፅሐፉ ውስጥ ለማመን የሚያዳግቱ የዓለም ዋንጫ ታሪኮችን ብቻ አይደለም የሰነደው፡፡ ይልቁንም ከመጀመሪያው የኡራጋይ ዓለም ዋንጫ እስከ ኳታር ያሉትን አስደናቂ፤ አስደማሚ፣ አዝናኝና ትንግርት የሚመስሉ እውነታዎችንና ገጠመኞችንም  ጭምር እንጂ፡፡  
በ20 የተለያዩ ቋንቋዎች በታተመው በዚህ መፅሐፍ ውስጥ ከተካተቱት ለማመን የሚያዳግቱ ታሪኮች መካከል፤ አንድ ደቡብ አፍሪካዊ የ2010 የዓለም ዋንጫ ነፃ ትኬቶችን ለማግኘት ሲል፣ አዞዎች በሞሉበት ወንዝ ውስጥ ዘሎ መግባቱ፤ አንድ የኡራጋይ ተጫዋች በድንገተኛ የልብ ድካም ከተጠቃ በኋላ ወደ ሜዳ ተመልሶ መግባቱ፤ እንዲሁም የሩሲያ  ጥንዶች “አሪፉ ተጫዋች ማነው፤ ሊዮኔል ሜሲ ወይስ ክርስቲያኖ ሮናልዶ?” በሚል ከተከራከሩ በኋላ መለያየታቸውን፤ የሚተርኩት  ተጠቃሽ ናቸው፡፡  
ከሮይተርስ ጋር ባደረገው ቃለመጠይቅ የዓለም ትልቁን የስፖርት ኹነት ከተለየ አንጻር እንደሚመለከተው የተናገረው ወርኒኪ፤ “ትናንሾቹ ታሪኮችም ቢሆኑ ዓለም ለእግር ኳስ ያለውን ጥልቅ ፍቅር የሚያሳዩ  ናቸው”  ብሏል።
ወርኒኪ እንዲህም ሲል ጽፏል፤ “እ.ኤ.አ በ1994 ዓ.ም አንድ አልባኒያዊ ወደ ውርርድ ቤት ይሄድና፣ አርጀንቲና ቡልጋሪያን ታሸንፋለች ብሎ ይወራረዳል፤ሚስቱንም በቁማር ያሲዛል። የማታ ማታ ታዲያ ያቺ የተወራረደላት አገር  2ለ0 በሆነ ውጤት ተሸነፈች፤ እሱም ውርርዱን ተበላ፤ በቁማር ያስያዛትን ሚስቱንም በአሳዛኝ ሁኔታ አጣ::” ይሄ ለማመን የሚያዳግት ታሪክ ሳይሆን “ጉድ” ነው መባል ያለበት፡፡
ከ16 ዓመት በኋላ ደግሞ የአስተናጋጇ አገር የደቡብ አፍሪካ አንድ የሬዲዮ ጣቢያ፤ የመጨረሻውን የዋንጫ ጨዋታ ሁለት ትኬቶች፣ ያልተለመደ የእብደት ድርጊት ለፈፀመ ሰው እንደሚሸልም ያውጃል፡፡ አሸናፊው ማን ቢሆን ጥሩ ነው? አዞዎች የሚርመሰመሱበት ወንዝ ውስጥ ዘሎ የገባ አንድ ሰውዬ ትኬቱን ወስዷል፤ይለናል ጸሃፊው፡፡  
በእያንዳንዱ የአለም ዋንጫ አዲስ ምዕራፍ እየታከለበት የሚበለፅገው “The Most Incredible World Cup Stories“ መፅሐፍ፤ ያሁኑ ሦስተኛው ዕትም ሲሆን ፀሃፊው ከኳታር የዓለም ዋንጫም ገና ካሁኑ ትናንሽ ጮማ ወሬዎችን እያሰባሰበ መሆኑ ተጠቁሟል፡፡
“ከአድማዎችና ከሰብአዊ መብት ጉዳዮች አንስቶ አያሌ ትኩረት የሚስቡ ነገሮች አሉ” ያለው ወርኒኪ፤ “ከስፖርት ውጭ በእርግጠኝነት በርካታ ጉዳዮች ይኖራሉ፡፡ የዘንድሮ የዓለም ዋንጫ ማህበራዊ ኹነቱ በእጅጉ የሚያመዝን ይሆናል” ብሏል፡፡
የአለም እግር ኳስ አድራጊ ፈጣሪ የሆነው ፊፋ፣ በወግ አጥባቂዋ የሙስሊም አገር ስቴዲዮሞች ቢራ እንደማይሸጥ ማወጁ፣ ለወርኒኪ ቀጣይ ምዕራፍ እንደ መነሳሻ ሊያገለግለው እንደሚችል ሮይተርስ በዘገባው ጠቆም አድርጓል፡፡
 የ53 ዓመቱ ሉቺያኖ ወርኒኪ የተወለደው በአርጀንቲና ቦን አይረስ ሲሆን ከሳልቫዶር ዩኒቨርሲቲ በጋዜጠኝነት ተመርቋል፡፡ ለ20 ዓመት ያህልም በ”Argentine University of Enterprise (UADE)” እንዲሁም በሌሎች ዩኒቨርሲቲዎች የስፖርት ጋዜጠኝነትን አስተምሯል፡፡ በበርካታ አገራትም መጣጥፎችን አሳትሟል፡፡ ከ20 በላይ የእግር ኳስና የስፖርት መፃህፍት ደራሲም ነው፡፡ ከመፃህፍቱ መካከልም የሚከተሉት ይጠቀሳሉ፡-
The Most Incredible world cup Stories(2010)
The Most Incredible World cup Stories(2012)
The most Incredible World cup Stories(2013)
Doctor and Champion (Autobiography of Carlos Bilardo-2014)
The Most Incredible Copa Libertadores Stories(2015)
Round Words (2016)
Why is Football played eleven against eleven? (2017)
Matador ( Autobiography of Mario Kempes -2017)
Duel Never Seen (2019)
Inside DIego (2021)
Football Drops (2022)
Dark Goals(2022)

Page 10 of 637