Administrator

Administrator

ተቃዋሚ ፓርቲዎች የመንግስትን ፖሊሲ ይተቻሉ
            በኢትዮጵያ ቆላማ አካባቢዎች የተከሰተውና ወደ 6 ሚሊዮን ገደማ ህዝብን ለአደጋ ያጋለጠው ድርቅ፤ህፃናት ተማሪዎችን ከትምህርት ገበታ ያናጠበ ሲሆን በመቶ ሺዎች የሚገመቱ ሰዎችንም ከቀዬአቸው አፈናቅሏል፡፡
ለበርካታ ዓመታት ይህን የድርቅ አደጋና ስጋት ማሸነፍና ማስወገድ ያልተቻለው ለምንድን ነው? ተቃዋሚ ፓርቲዎች በዚህ አገራዊ ችግር ላይ አማራጭ የመፍትሄ ሀሳብ ሲያቀርቡ እምብዛም አይስተዋልም፡፡
በወቅታዊው የድርቅ አደጋና ስጋቱ እንዲሁም በዘላቂ መፍትሄዎች ዙሪያ የአዲስ አድማስ ጋዜጠኛ አለማየሁ አንበሴ የተቃዋሚ ፓርቲ አመራሮችን አነጋግሯል፡፡

              “መንግስት ስለ ድርቁ ትክክለኛ መረጃ ሊያቀርብልን ይገባል”
                                 አቶ የሸዋስ አሰፋ (የሠማያዊ ፓርቲ ሊቀመንበር)

       መንግስት ለተፈጠረው ድርቅ የሰጠው ትኩረት በኛ ፓርቲ በኩል አነስተኛ ነው የሚል ግምገማ ነው ያለን፡፡ ከ800 በላይ ት/ቤቶች ተዘግተው፤ በርካቶች ተሰደዋል ግን ስለ ጉዳዩ ብዙ ሲባል አይሰማም፡፡ ይሄ መደባበቅ ነው፡፡ ያለፉ መንግስታት ሲተቹ የነበረውኮ በዚህ የተነሳ ነው፡፡ መንግስት ችግሩን በቅጡ እንድናውቀው አላደረገንም፡፡ አሁን እንደ መረጃ የምንጠቀመው አለማቀፍ ተቋማት የሚያወጡትን ሪፖርት ነው፡፡ ይሄ ትክክል አይደለም፡፡ መንግስት ጉዳዩን ሁሉም አውቆት የድርሻውን እንዲወጣ ማድረግ አለበት፡፡
ሰማያዊ ፓርቲ በድርቅ በተጎዱ አካባቢ ያሉ ሰዎችን አነጋግሮ መረጃ ለማግኘት ሞክሮ ነበር፡፡ እንደተረዳነው፤ በጥቅምት መዝነብ የነበረበት ዝናብ ባለመዝነቡ በውሃና በግጦሽ እጦት ከብቶቻቸው እንዳለቁባቸውና እነሱም ለከፋ ችግር እንደተጋለጡ ነው፡፡ በፓርቲያችን እምነት፤ በተደጋጋሚ በድርቅ ለሚጠቁ መሰል አካባቢዎች የሚሆን ተስማሚ ፖሊሲ አለመቀመጡ አደጋውን እስከ ዛሬ ላለመሻገራችን ምክንያት ነው፡፡ 6 ሚሊዮን ህዝብ በድርቅ ተጎዳ ማለት፣ የአንድ ሀገር ህዝብ ያህል ነው፡፡ ይሄን እንኳ በአግባቡ መንግስት ሊገልፀው አልፈለገም፡፡ ተቃዋሚዎች በጉዳዩ ላይ ትኩረት አድርገን፣ መንግስት ላይ ጫና እንዳናሳድር በአሁኑ ወቅት  በብዙ ጉዳዮች ተጠምደናል፡፡ በዚህ ሳምንት እንኳ 12 ሰዎች ታስረውብናል፡፡ ግን ቀንና ቀጠሮ የማይጠይቀው ይሄ ጉዳይ በሚገባው መጠን ንቅናቄ አልተደረገበትም፡፡ ምናልባት መንግስትም ሀገርም በብዙ ችግር መዋጣቸው፣ለጉዳዩ ትኩረት እንዳይሰጠው ማድረጉን አምናለሁ፡፡ ይሄ ትክክል አይደለም፡፡ የእነዚህ ህፃናት፣ ሴቶችና አዛውንቶች በድርቅ የመጎዳት ጉዳይ ቅድሚያ ትኩረት ተሰጥቶት ርብርብ ሊደረግበት ይገባል፡፡ አሁንም መንግስት ከምንም በላይ ቅድሚያ እንዲሰጠው ፓርቲያችን በአቋም መግለጫው አሳስቧል፡፡ መንግስት በችግር ውስጥ ላሉ ዜጎቻችን ከምንም በላይ ቅድሚያ ሰጥቶ፣የመታደግ ስራ ላይ መረባረብ አለበት፡፡
ድርቁ ራሱ መኖሩ ችግር አይደለም፤ ድርቁ ረሃብ ሲፈጥር ግን በግልፅ የመንግስት ፖሊሲ ችግር እንዳለ ያስረዳል፡፡ ለፖሊሲ ውድቀት ከዚህ በላይ ማስረጃ አይገኝም፡፡ በየ10 ዓመቱ ድርቅ እንደሚመጣ ይታወቃል፤ ለምን በቂ ዝግጅት አይደረግም? ዛሬ ከ800 በላይ ት/ቤቶች ተዘግተው፣ እንዴት ችግር ሳይፈጥር ድርቁን እየተቋቋምኩ ነው የሚል ሪፖርት ይሰጣል? ይሄ በቂ የአደጋ መከላከል ዝግጅት እንዳልተደረገ ማሳያ ነው፡፡ ጊዜያዊ መፍትሄዎችን ማስቀመጥ ያስፈልጋል፡፡ እንደ ፓርቲያችን መደረግ ያለበት ብለን የምናምነው፣በተለይ በተደጋጋሚ በድርቅ በሚጎዱ አካባቢዎች የሚኖሩ ዜጎችን ውሃ ወዳለበት የሀገሪቱ አካባቢ ማሰባሰብ ነው፡፡ በቀጣይ አርብቶ አደሩ በአንድ ምቹ አካባቢ ተረጋግቶ በመቀመጥ ወደ ከፊል አርሶ አደርነት እንዲለወጥ ተከታታይ ስራዎች መሰራት አለባቸው የሚለው ነው፡፡ ከመፍትሄዎቹ መካከል እነዚህ እንደ አማራጭ የሚቀመጡ ናቸው፡፡ ነገር ግን አሁን ለአስቸኳዩ ችግር ሁሉም አካላት ትኩረት ሰጥተው ሊሰሩ ይገባል፡፡ መንግስት ስለ ድርቁ ጉዳይ ትክክለኛ መረጃ ሊያቀርብልን ይገባል፡፡ ሀቆች መደበቅ የለባቸውም፡፡

------------------

                        ‹‹ድርቅም ቢኖር ረሃብ ሊኖር አይገባም››
                        ዶ/ር ጫኔ ከበደ
                           (የኢዴፓ ፕሬዚዳንት)

       በአሁኑ ወቅት የተከሰተውን ድርቅ አስመልክቶ ፓርቲዎች መንግስት ላይ ግፊት አላደረጉም፤ ነገር ግን በፓርቲዎች የጋራ ምክር ቤት በኩል አጀንዳው ተነስቶ ውይይት ተደርጎበት ጥናት እንዲደረግ ተወስኗል፡፡ በዚህ ደረጃ የሚመጣውን ውጤት እንጠብቃለን፡፡
በአቋም ደረጃ ግን ፓርቲያችን ከሚያራምደው ፕሮግራም አንፃር፣ ኢትዮጵያ በተደጋጋሚ እንዲህ ያለው ድርቅ ሊያጠቃት የቻለው በአየር ፀባይ ለውጥ ምክንያት ሊሆን ይችላል፤ነገር ግን ድርቅም ቢኖር ረሃብ ሊኖር አይገባም የሚል አቋም ነው ያለን። ሌሎች ሃገሮች ከዚህም የከፋ ድርቅ ይመታቸዋል፤ ነገር ግን ዜጎቻቸው ሲራቡ አይተንም ሰምተንም አናውቅም፡፡ የፓርቲያችን ፕሮግራም በሊበራል የኢኮኖሚ ሲስተም የሚመራ እንደመሆኑ፣ እንዲህ ያሉ ችግሮችን ለመቋቋም ራስን በሚያስችል የመስኖ ልማት ውስጥ መገባት አለበት። ወንዞቻችን ከኛ አልፈው ለሌላው የሚተርፉ ናቸው።
ድርቅን ተከትለው የሚከሰቱ ችግሮችን መቋቋም አለመቻላችን የሚያሣየን፣ መንግስት በመስኖ ልማት የዚህችን ሃገር ዘላቂ የምግብ ዋስትና ለማረጋገጥ በሚገባው መጠን በቁርጠኝነት እየሰራ አለመሆኑን ነው፡፡ ድርቅን ተቋቁሞ ረሃብን ማጥፋት በሚቻልበት ዙሪያ ብዙ እንዳልተሰራ በየአመቱ ድርቅን ተከትሎ እየተፈጠሩ ያሉ ችግሮች አስረጅ ናቸው፡፡
መንግስት ለሌሎች ሜጋ ፕሮጀክቶች እንደ ኢነርጂ ላሉት ትልቅ ትኩረት ሲሰጥ እናያለን፤ ነገር ግን በመስኖ ልማት ላይ የጠነከረ ስራ ሲሰራ አይታይም። ይህ መንግስት ከሚከተለው የልማት ፖሊሲ ደካማነት የመነጨ ነው፡፡ የሃገሪቱን ሃብቶች አሟጦ ከመጠቀምና ህዝቡን ከመሰል ችግሮች በዘላቂነት ከመታደግ አንፃር፣ አሁን መንግስት እየተከተለ ያለው ፖሊሲ የተሳሳተ ነው፡፡ በአሁኑ ሰአት ለሃገሪቱ ጠቃሚ የሚሆነውና ህዝብን ከድርቅ አደጋ መታደግ የሚቻለው ለሌሎች ልማቶች የተሰጠውን ትኩረት ያህል ለትላልቅ የመስኖ ልማቶች ሲሰጥ ብቻ ነው የሚል አቋም አለን፡፡ ይሄን ማድረግ እስካልቻልን ድረስ ተፈጥሮ በየጊዜው እየተዛባ ባለበት ሁኔታ ህዝብን ከችግር መታደግ አይቻልም፡፡ በኢኮኖሚ እድገቱ ላይም የራሱን አሉታዊ ተፅእኖ ያሳርፋል። ያለንበትን ጂኦግራፊያዊ ሁኔታ በሚገባ በጥናት በመለየት ለየዘርፉ ችግሮች ተመጣጣኝ የመፍትሄ አቅጣጫዎች ማስቀመጥ ያስፈልጋል፡፡
ህዝቡ በመስኖ ልማት ውስጥ እንዲሳተፍ ሰፊ ስራ መሰራት አለበት፡፡ ለምሳሌ በድርቅ ከተጎዱት የአንበሳውን ድርሻ የሚይዘው የሶማሌ ክልል ነው። ወደዚያ አካባቢ የሄደ ሰው በእጅጉ ያዝናል፡፡ ያንን የመሰለ ለም መሬት አቋርጠው ወደ ጎረቤት ሶማሊያ የሚፈሱ ወንዞችን ሲያይ በእጅጉ ይቆጫል፡፡ በጣም ነው የሚያስቆጨው፡፡
ወንዞቹ ያንን የመሰለ ለመስኖ ልማት ተስማሚ የሆነ ለም መሬት አቋርጠው ሶማሊያ ገብተው ጥቅም ሲሰጡ ለተመለከተ፣ በእርግጥስ ምንድን ነው ችግሩ የሚል ጥያቄ ያጭርበታል፡፡ ዛሬ ሶማሊያ ከምስራቅ አፍሪካ አንደኛ የሙዝና የብርቱካን አቅራቢ የሆነችው፣ የኛን ለም መሬት አቋርጠው የሚሄዱ ወንዞችን ለመስኖ በመጠቀሟ ነው እንጂ ዝናብ የላትም፡፡ እኛ ከባሌ ተራራዎች እየፈለቁ ሶማሌ ክልልን እያቋረጡ የሚሄዱ ወንዞችን ሳንጠቀም፣ ሁልጊዜ የሶማሌ ክልል ህዝብ ተራበ የሚል ሪፖርት ነው የምንሰማው፡፡
ክልሉ ካለው ሰፊ የተፈጥሮ ፀጋ አንፃር እዚያው ሰብሉ ለምቶ፣ እዚያው በአግሮ ፕሮሰሲንግ እሴት የተጨመረባቸውን ምርቶች በማምረት ትልቅ የምግብ ምርት አካባቢ ማድረግ በተቻለ ነበር፡፡ ግን በመንግስት የተሳሳተ ፖሊሲና ትኩረት ማነስ የተነሳ ይሄ እውን ሊሆን አልቻለም፡፡ ዛሬ በድርቅ አዙሪት ውስጥ ለመዳከራችንም ይሄው ነው ዋነኛ ምክንያቱ፡፡

---------------

                        “በድርቅ ለተጎሳቆለ ህዝብ አስፋልት ቢዘረጋለት ምኑ ነው?”
                                ፕ/ር በየነ ጴጥሮስ (የመድረክ ሊቀመንበር)

        ድርቅ ስለመኖሩና በዚህ ምክንያት በህዝብ ላይ ጉዳት እየደረሰ ስለመሆኑ ይሄ መንግስት ለአለማቀፉ ማህበረሰብ መረጃ ለማድረስ ትንሽ ይተናነቀዋል፡፡ መጀመሪያ ምንም ጉዳት እንደሌለ ተገልፆ ነው፣ ቀስ በቀስ የጉዳቱ መጠን ቁጥሩ እየጨመረ የሚሄደው። “ሀገሪቷ አድጋለች ብዙ ለውጠናታል፤እንዴት ስለ ድርቅ ይወራል” በሚል መንግስት እውነታውን ለመናገር ድፍረት ያንሰዋል፡፡ እውነቱ ግን ይህቺ ሀገር ከድርቅ ጉዳት ለመላቀቅ የሚያስችል ስራ አልተሰራባትም። መንግስት መረጃ አሰጣጡ ላይ መታረም አለበት፡፡ በየዓመቱ ተመላልሶ የሚመጣ እንደመሆኑ ድርቁ ተተንባይ ነው፡፡ በዚህ ተተንባይ በሆነና የራሱ የታወቀ ጊዜ ባለው የተፈጥሮ አደጋ፣ ለምን ዜጎቻችን ይጎዳሉ? የሚለው በእውነቱ አነጋጋሪ ነው፡፡ ሁሉም ወገን ለዚህ ቅድሚያ ሰጥቶ በትኩረት መስራት አለበት፡፡ ብዙ ገንዘብ በተለያዩ ብድሮችና እርዳታዎች እየመጣ፣ እዚያም እዚህም ሲበተን እናያለን፡፡
ከ6 ሚሊዮን በላይ ህዝብን ከረሃብ ስጋት የሚያወጣ በቂ ስራ እስከዛሬ አለመሰራቱ በእውነት አስተዛዛቢ ነው። ለህዝቡና ለከብቶቹ በየቦታው ውሃ ማውጣት እንዴት ይከብዳል? ይሄ ከሁሉም መሰረት ልማት ቅድሚያ ተሰጥቶት መታሰብ ያለበት ጉዳይ ነው፡፡
ለእነዚህ አይነት አካባቢዎች መሰረት ልማት ማለት በዋናነት መንገድ ብቻ አይደለም፤ ቅድሚያ ሊሰጠው የሚገባው ውሃ ነው፡፡ የህዝቡ አኗኗር በእንስሳት ሃብት ላይ ጥገኛ የሆነ ነው፡፡ ለሱም ለከብቶቹም ውሃ ማግኘት አለበት፡፡ ይሄን መስራት እንዴት ይከብዳል? ውሃ ማቆር እየተባለ እንደ ፋሽን አንድ ሰሞን ይወራል፤ከዚያ እንደዘበት ይቀራል፡፡ አስፋልት ከሚለብሱ መንገዶች በፊት መጀመሪያ የሰው ህይወት መቅደም አለበት፡፡ ይሄንን ባለማድረግ መንግስት ትልቅ በደል እየፈፀመ ነው የሚል ነው የኛ አቋም፡፡
ውሃ አጠር ለሆኑ አካባቢዎች ውሃ ማቅረብ ከሁሉም ቅድሚያ ሊሰጠው ይገባል፡፡ ለእንስሳትም ለሰውም ምግብ በበቂ ሁኔታ መድረስ አለበት፡፡ በቂ የእህል ክምችት አለን እየተባለ ነው፤ ታዲያ ለምን ህፃናት ተጎሣቁለው ትምህርት ያቋርጣሉ? ይሄ በእውነት ሊታሰብበት ይገባል፡፡ ከሁሉ በፊት ዜጎችን ከዚህ ጉስቁልና ማውጣት ያስፈልጋል። በድርቅ ለተጎሳቆለ ህዝብ ውሃ የመሰለ አስፓልት በአጠገቡ ቢዘረጋለት ምንም ስሜት አይሰጠውም፡፡ ለቪዲዮ ቀረፃ ብቻ የሚመቹ መሰረተ ልማቶችን መገንባት ሳይሆን በሚሊዮኖች የሚቆጠሩ ዜጎችን የመኖር ዋስትና ማስጠበቅ ያስፈልጋል፡፡

-----------------

                        “መንግሥት ዘላቂ መፍትሄ ማፈላለግ አለበት”
                          ዶ/ር በዛብህ ደምሴ (የመኢአድ ፕሬዚዳንት)

       በ1966 እና በ1977 በዚህች ሀገር ያጋጠመው ድርቅ፣ ዜጎችን ለከፋ ረሃብ ዳርጎ፣ የዓለም ህዝብ ታድጎናል፡፡ በ1966 ለአፄ ኃይለ ሥላሴ ውድቀት ከፍተኛ አስተዋፅኦ የነበረው ድርቁና ረሀቡ ነው፡፡ ደርግም በድርቅ ብዙ ተፈትኗል፡፡ ይሄም መንግስት እየተፈተነ ነው፡፡ ዜጎች ዛሬም የረሃብ ስጋት ላይ በመውደቃቸው የእርዳታ እጅ ተዘርግቷል፡፡ በሌላ በኩል ለፖለቲካ ተብሎ የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ ታውጇል፡፡ ግን አስቸኳይ ጊዜ አዋጁ የሚገባው ለድርቁ ነው፡፡ መንግስት አሁን እየተቸገሩ ላሉት 6 ሚሊዮን ገደማ ዜጎቻችን እርዳታ እያቀረብኩ ነው ይላል፤ህዝቡ ደግሞ እየተራብኩ ነው ሲል በተለያዩ የመገናኛ ብዙኃን እየሰማን ነው፡፡ አሁን የሚያስፈልገው ከፖለቲካውም ጉዳይ ይልቅ ቅድሚያ ሰጥቶ በዚህ ችግር ላይ ርብርብ ማድረግ ነው፡፡ ተቃዋሚዎችም ጭምር፡፡
ፕ/ር በየነ ጴጥሮስ በሚመሩት አማራጭ ኃይሎች ፓርቲ ውስጥ በነበርኩ ጊዜ በወቅቱ በሀገሪቱ ተከስቶ ለነበረው ድርቅ፣ እርዳታ አሰባስበን ለማቅረብ ለመንግስት ጥያቄ አቅርበን ነበር፤ሆኖም ከመንግስት ቀና ምላሽ አላገኘንም ነበር፡፡ ሁሉም ነገር በፖለቲካ አይን መታየት የለበትም፡፡ ሠብአዊ ድጋፍ የፖለቲካ አቋም አይወስነውም፡፡
መንግስት ከጊዜያዊ እርዳታ ባለፈ በዘላቂ መፍትሄዎች ዙሪያ አማራጭ ሃሳቦችን ከተቃዋሚዎች መቀበል አለበት፡፡ ለምሳሌ ለምንድን ነው ዝናብ ጠባቂ የምንሆነው? ለምን ሰፋፊ መስኖ አይሰራም? ከሁሉም መሰረት ልማቶች ይሄ መቅደም አለበት፡፡ የውሃ አቅማችን ከፍተኛ ነው፤ለምን ይሄን ሃብት ለህዝባችን ጥቅም አናውለውም? ይሄ እስካሁን ምላሽ ያላገኘ ጥያቄ ነው፡፡
የዛሬ 40 ዓመት ሩሲያ ሃገር ተማሪ በነበርኩ ሰአት አንድ የሩሲያ ፀሃፊ ስለ ኢትዮጵያ ባዘጋጀው መፅሃፍ ላይ፣ኢትዮጵያን የአፍሪካ ገነት ይላታል፡፡ “ሃገሪቱ ባላት የተፈጥሮ ሃብት ራሷን ከመገበች በኋላ ለትላልቅ 6 መንግስታት ህዝቦች የሚበቃ የእርሻ ምርት የማቅረብ አቅም ያላት ናት” ሲል በሰፊው ተንትኖ ፅፏል፡፡ እንግዲህ ዋናው ችግራችን ጥሩና ተስማሚ የፖሊሲ አማራጮችን በሚገባ ፈትሾ በስራ ላይ አለማዋል ነው፡፡  

----------------

                        “ከፖለቲካ በፊት የዜጎችን ህይወት መታደግ ይቀድማል”
                           አቶ ተሻለ ሰብሮ (የኢራፓ ፕሬዚዳንት)

       ከምንም በላይ የህዝብ አድን ስራዎች ቅድሚያ ሊሰጣቸው ይገባል የሚል አቋም አለው፤ ፓርቲያችን፡፡ በየጊዜው ይህ ድርቅና ረሃብ መከሰቱ በእጅጉ አሳዛኝ ነው፡፡ እስከዛሬም አለመቆሙ ሁነኛ መፍትሄ እንዳልተበጀለት አመላካች ነው፡፡ ድርቅን መቋቋም በሚቻልበት ጉዳይ ላይ በቂ ልምድ እንዳልተቀሰመም መታዘብ ችለናል፡፡
ለምሳሌ እስራኤልና ግብፅ በረሃማ አካባቢን እንዴት ለሰው ልጆች እንዲመች አድርጎ መግራት እንደሚቻል ማሳያዎች ናቸው፡፡ እነዚህን ልምዶች በመቅሰም በሃገራችን ልንሰራበት ይገባ ነበር፡፡ ችግሩ በተፈጠረ ቁጥር የነፍስ አድን ስራ ላይ ብቻ መረባረብ ውጤት የለውም፡፡ ከዚያ ይልቅ የፖሊሲ ጥናት ተደርጎ፣ በልዩ ትኩረት አዋጭና ዘላቂ ስራዎችን መስራት ያስፈልጋል፡፡ ብዙ ጊዜ በፖለቲካ መጠላለፍና አተካሮ ሲኖር፣ እንዲህ ያሉ ወሳኝ የህዝብ ጉዳዮች ይዘነጋሉ፡፡ ዘንድሮ ወደ 6 ሚሊዮን የሚጠጋ ህዝብ በድርቅ አደጋ ላይ ሆኖ ትኩረት ያልተሰጠው በዚህ ምክንያት ነው፡፡  
መንግስትም፣ ተቃዋሚዎችም ሆኑ ሌሎች ባለድርሻ አካላት ይሄን በብሄራዊ መግባባት ማጤን አለባቸው። ከፖለቲካ በፊት የሰው ህይወትን መታደግና ዘላቂ ዋስትና ማስገኘት ይቀድማል፡፡ ተቃዋሚዎች ይሄን ጉዳይ መንግስት ትኩረት ሰጥቶት፣ህዝቡን እንዲታደግ ግፊት ማድረግ አለብን፡፡ አሁን እንኳ በተጀመረው ድርድር፣ ስለ ድርቅ አደጋ ምን ያህል ትኩረት ተሰጥቶት፣ በአጀንዳነት ለመወያየት ታስቦ እንደሆነ አናውቅም። ግን ይሄ የህዝባችን ዋነኛ ችግር ነው፡፡ ከፖለቲካም በላይ ነው፡፡ ይህ ተደጋጋሚ ችግር እንዴት እስከዛሬ ዘላቂ መፍትሄ አልተገኘለትም? ሰፊ ክርክርና ውይይት ሊደረግበት የሚገባ ወሳኝ ሃገራዊ ጉዳይ ነው፡፡ በአባይ ጉዳይ ላይ ያለንን ሃገራዊ መግባባት በድርቅ ጉዳይ ላይ አናስተውልም፡፡
የዜጎችን ህይወት መታደግ ከአባይ ጉዳይም በላይ ነው፡፡ የተለያዩ ፖሊሲዎችና የመፍትሄ ሃሳቦች ቀርበው ሰፊ ክርክርና ውይይት ማድረግ አለብን፡፡ በብሄራዊ ደረጃ ይሄን የሚያስፈፅም ትልቅ ንቅናቄ ያስፈልጋል፡፡

   42ኛው የዓለም አገር አቋራጭ ሻምፒዮና ከሳምንት በኋላ በኡጋንዳዋ ከተማ ካምፓላ አስተናጋጅነት የሚካሄድ ሲሆን፤ 66 አገራትን የወከሉ ከ600 በላይ አትሌቶች በአምስት አይነት የአገር አቋራጭ ውድድሮች ይሳተፉበታል፡፡ በሻምፒዮና ከፍተኛውን የውጤት ግምት ያገኙት የኢትዮጵያ እና የኬንያ አትሌቶች ናቸው። የኢትዮጵያ አትሌቲክስ ፌደሬሽን ለሻምፒዮናው ከ1 ወር በላይ ዝግጅት ሲያደርግ ቆይቷል፡፡ የኢትዮጵያ ሙሉ የቡድን ዝርዝር ባይታወቅም፤ በ34ኛው የጃንሜዳ ኢንተርናሽናል አገር አቋራጭ በሁሉም የውድድር መደቦች ከ1 እስከ 4 ደረጃ ያገኙት እንዲሁም በወቅታዊ ብቃታቸው እና የጤንነት ደረጃ አስተማማኝ ሆነው የተገኙትን በ5ኛ እና በ6ኛ ደረጃ ለማካተት 40 አትሌቶች በዓለም አገር አቋራጭ ቡድኑ ጊዜያዊ ዝርዝር ተካትተዋል፡፡ በወንዶች ምድብ እነ ሙክታር ኢድሪስ፤  ኢብራሂም ጄይላን እንዲሁም ዮሚፍ ቀጀልቻ በሴቶች ደግሞ ገንዘቤ ዲባባ ልምድ ካላቸው ምርጥ አትሌቶች ይጠቀሳሉ፡፡ በ9 አሰልጣኞች እና ረዳቶቻቸው እየተዘጋጀ የሚገኘው  ቡድኑ በአራራት ሆቴል ተቀምጦ ከሚያደርጋቸው ስልጠናዎች ባሻገር በአዲስ አበባ ዙርያ በሚገኙ ትንንሽ ከተሞች የጎዳና ላይ እና የጫካ ልምምዶች እያደረገም ነው፡፡ ሁለቱ የምስራቅ አፍሪካ አገራት በተለይ በረጅም ርቀት ውድድሮች በወንዶች ከ1981 እኤአ ጀምሮ እንዲሁም በሴቶች ከ1991 እኤአ ጀምሮ ሌሎች አገራትን ጣልቃ ሳያስገቡ በአሸናፊነቱ ላይ ተፈራርቀዋል፡፡ ከኢትዮጵያ እና ኬንያ ባሻገር በተለይ በአዋቂዎች ምድብ ምናልባትም በግል ውጤታማ ሊሆኑ የሚችሉ አትሌቶችን እንደሚያሰልፉ የተወሳላቸው ከአፍሪካ አዘጋጇ ኡጋንዳ እና ኤርትራ እንዲሁም የቱርክ፤ የባህሬን፤ የአሜሪካ፤ የእንግሊዝ፤ የአየርላንድ እና የጃፓን አትሌቶች ናቸው፡፡ ውድድሩን የምታስተናግደው የካምፓላ ከተማ በዓለም አቀፍ ደረጃ የሚያስፈልገውን ቅድመ ዝግጅት ማጠናቀቋን አረጋግጧል፡፡ ሻምፒዮናውን የሚያስተናግደው በ2014 እኤአ ላይ የአፍሪካ የዓለም አገር አቋራጭ ሻምፒዮናን ያስተናገደው የስፖርት ማእከል እንደሆነ ሲታወቅ፤ በከፍተኛ እድሳት ለውድድሩ መዘጋጀቱን ለማወቅ ተችሏል፡፡ በሌላ በኩል  አይኤኤኤፍ እውቁን የኬንያ አትሌት ፖል ቴርጋ የዓለም አገር አቋራጭ ሻምፒዮና አምባሳደር አድርጎ ሾሞታል፡፡ በአይኤኤኤፍ እና በዓለም አቀፉ ኦሎምፒክ ኮሚቴ አባልነት የሚያገለግለው ፖል ቴርጋት በዓለም አገር አቋራጭ ከፍተኛ ውጤት ካመዘገቡ አትሌቶች አንዱ ሲሆን ለአምስት ጊዜያት በረጀም ርቀት 12 ኪሎ ሜትር በማሸነፍ የወርቅ ሜዳልያዎቹን ሰብስቧል፡፡ በዓለም አገር አቋራጭ ሻምፒዮናው  ታሪክ ለመጀመሪያ ጊዜ በሁለቱም ጾታዎች ድብልቅ የዱላ ቅብብል ውድድር እንደሚኖርም ታውቋል፡፡ ዓለም አቀፉ የእግር ኳስ ፌደሬሽኖች ማህበር በሻምፒዮናው በግልና በቡድን  ከ1ኛ እስከ 6ኛ ደረጃ ለሚያገኙ አትሌቶች እና አገራትም የገንዘብ ሽልማት ያበረክታል።  በአዋቂ አትሌቶች የሁለቱም ፆታዎች የውድድር መደቦች በግል  ውጤት ለሚያስመዘግቡ አትሌቶች ለ1ኛ 30ሺ ዶላር፣ ለ2ኛ 15ሺ ዶላር፣ ለ3ኛ 10ሺ ዶላር፣ ለ4ኛ 7ሺ ዶላር፣ ለ5ኛ 5ሺ ዶላር እንዲሁም ለ6ኛ ደረጃ 3ሺ ዶላር ይበረከታል፡፡ በቡድን ውጤት ለሚያሸንፉ አገራት ደግሞ ለ1ኛ 20ሺ ዶላር፣ ለ2ኛ 16ሺ ዶላር፣ ለ3ኛ 12ሺ ዶላር፣ ለ4ኛ 10ሺ ዶላር፣ ለ5ኛ 8ሺ ዶላር እንዲሁም ለ6ኛ ደረጃ 4ሺ ዶላር የሚታሰብ ሲሆንበሁለቱም ፆታዎች ድብልቅ የዱላ ቅብብል ውድድር ለ1ኛ 12ሺ ዶላር፣ ለ2ኛ 8ሺ ዶላር፣ ለ3ኛ 6ሺ ዶላር፣ እንዲሁም ለ4ኛ 4ሺ ዶላር እንደሚሸለም ለማወቅ ተችሏል፡፡
በ2021 እ.ኤ.አ የ44ኛው የዓለም አገር አቋራጭ አዘጋጅነት ለኢትዮጵያ?
የዓለም አገር አቋራጭ ሻምፒዮና በአይ.ኤ.ኤ.ኤፍ ስር ከሚካሄዱ ውድድሮች በአንጋፋነቱ እና በፈታኝነቱ የሚጠቀስ ነው፡፡  ከ1973 እኤአ ጀምሮ የዓለም አገር አቋራጭ ሻምፒዮናው ለ38 ጊዜያት በየዓመቱ ሲካሄድ የነበረ ሲሆን፤ ከ2011 እ.ኤ.አ ወዲህ ግን በየሁለት ዓመቱ የሚደረግ ሆኗል፡፡ በተለይ ባለፉት 25 አመታት የምስራቅ አፍሪካ አትሌቶች በየውድድር መደቡ እስከ 10 ያለውን ደረጃ በከፍተኛ ሁኔታ በመቆጣጠር ያሳዩት የበላይነት  ባስከተለው ጫና ነው፡፡ የዓለም አገር አቋራጭ ሻምፒዮናው በየሁለት ዓመቱ መካሄድ ከጀመረ ዘንድሮ 5ኛው  ነው ማለት ነው፡፡ በዓለም አገር አቋራጭ ሻምፒዮና ላይ ኢትዮጵያ በተሳትፎ ታሪኳ  ታላላቅ ውጤቶችን አስመዝግባለች፡፡ በኦሎምፒኮችና በዓለም አትሌቲክስ ሻምፒዮናዎች ታላላቅ ስኬት ያገኙ አትሌቶች የተገኙት ከፈታኙ የአገር አቋራጭ ሩጫ እንደሆነ ይታወቃል፡፡ ዘንድሮ የሻምፒዮናውን መስተንግዶ በጐረቤቷ የምስራቅ አፍሪካ አገር ኡጋንዳ መቀደሟ የሚያስቆጭ ይመስላል፡፡    ሻምፒዮናውን በአፍሪካ አገር ሲካሄድ የዘንድሮው የኡጋንዳ፤ ካምፓላን መስተንግዶ ጨምሮ ለ5ኛ ጊዜ ሲሆን ሞሮኮ ለሁለት ጊዜያት በ1975 እና በ1998 እኤአ፤ ደቡብ አፍሪካ በ1996 እኤአ እንዲሁም ኬንያ በ2007 እኤአ የዓለም አገር አቋራጭ ሻምፒዮናውን አዘጋጅተዋል። ከአውሮፓ እንግሊዝ፤ ፖላንድ፤ ፈረንሳይ፤ ስፔን፤ ፖርቱጋልና ጣልያን ከአንድ ጊዜ በላይ ውድድሩን ያስተናገዱ ከተሞች ሲሆኑ፤ አሜሪካም ከአንድ ግዜ በላይ አዘጋጅ ነበረች፡፡ ከኤስያ ጃፓን፤ ከመካከለኛው ምስራቅ ጆርዳን ሁሉ የዓለም አገር አቋራጭ ሻምፒዮናን አስተናግደዋል፡፡ በዓለም አገር አቋራጭ ሻምፒዮና የተሳትፎ ታሪክ ከፍተኛውን ውጤት በማስመዝገብ የምትጠቀሰው ኢትዮጵያ ውድድሩን የማዘጋጀት እድሏ ሰፊ በመሆኑ በዚህ አቅጣጫ ትኩረት አድርጎ መስራት ያስፈልጋል፡፡ ከኡጋንዳዋ ካምፓላ ከተማ በኋላ በ2019 እኤአ ላይ 43ኛውን የዓለም አገር አቋራጭ ሻምፒዮና እንድታዘጋጅ የዴንማርኳ አሩውስ ከተማ የተመረጠች ሲሆን፤  የኢትዮጵያ አትሌቲክስ ፌደሬሽንና ሌሎች ባለድርሻ አካላት ቢያንስ   በ2021 እ.ኤ.አ ላይ 44ኛውን የዓለም አገር አቋራጭ ሻምፒዮናን ለማስተናገድ ጥረት ማድረግ ይኖርባቸዋል፡፡
የኢትዮጵያ ውጤት ታሪክ ባለፉት 41 የዓለም አገር አቋራጭ ሻምፒዮናዎች
ባለፉት 41 የዓለም አገር አቋራጭ ሻምፒዮናዎች ላይ በሁለቱም ፆታዎች በአዋቂዎች እና በወጣቶች የውድድር መደቦች የቡድን ውጤት ከቀረቡ 168 ሽልማቶች ኢትዮጵያ  123ቱን ማግኘት የቻለች ሲሆን፤ በአዋቂዎች ምድብ በሁለቱም ፆታዎች በተለይ በረጅም ርቀት ውድድሮች    19  የወርቅ ሜዳልያዎችን አስመዝግባለች።  በሻምፒዮናው የኢትዮጵያ የተሳትፎ ታሪክ በአዋቂዎች ምድብ የአጭርና ረጅም ርቀት ውድድሮች ድርብ የወርቅ ሜዳልያዎች በማግኘት የመጀመሪያው የኢትዮጵያ አትሌት  ቀነኒሣ በቀለ ነው። ቀነኒሣ በአጭር ርቀት 4 ኪ.ሜ እና በረጅም ርቀት 12 ኪ.ሜ ውድድሮች በ5 ሻምፒዮናዎች በተከታታይ በማሸነፍ ብቸኛው አትሌት ሲሆን በ2008 እ.ኤ.አ ላይ በረጅም ርቀት 6ኛውን የወርቅ ሜዳልያ በማግኘቱ ደግሞ በዓለም አገር አቋራጭ ሻምፒዮናው ታሪክ ከፍተኛውን የውጤት ክብረወሰን ያስመዘገበ አትሌት ሆኗል፡፡ በሌላ በኩል በዓለም አገር አቋራጭ ሻምፒዮናው በአዋቂዎች ምድብ ውጤታማ ከሆኑ የኢትዮጵያ ሴት አትሌቶች መጠቀስ ያለባቸው ደራርቱ ቱሉ፤ ጌጤ ዋሚ፤ ጥሩነሽ ዲባባ፤ ወርቅነሽ ኪዳኔ ዋናዎቹ ናቸው፡፡  አትሌት ደራርቱ ቱሉ በረጅም ርቀት ለ3 ጊዜያት ያሸነፈች ሲሆን፣ ጥሩነሽ ዲባባ ደግሞ በአዋቂዎች ምድብ በረጅም ርቀት ለ3 ጊዜያት እንዲሁም በአጭር ርቀት 1 ጊዜ ማሸነፍ ከኢትዮጵያ ሴት አትሌቶች ትልቁን ውጤት አስመዝግበዋል፡፡
በዓለም አገር አቋራጭ ሻምፒዮና ላይ በኢትዮጵያዊ አትሌት የመጀመሪያው የሜዳልያ ድል የተመዘገበው በ1981 እ.ኤ.አ ላይ በአዋቂዎች ምድብ በወንዶች የ12 ኪ.ሜ ውድድር ሲሆን መሃመድ ከድር ባገኘው የብር ሜዳልያ ነው፡፡ አትሌት መሐመድ ከድር ከዓመት በኋላ በ1982 እኤአ በተመሳሳይ ረጅም ርቀት አሸንፎ የመጀመሪያውን የወርቅ ሜዳልያ ለኢትዮጵያ አስገኝቷል፡፡ በአዋቂ ወንዶች የ12 ኪሎሜትር ውድድር ኢትዮጵያ ከሰበሰበቻቸው 10 የወርቅ ሜዳልያዎች ስድስቱን ያስመዘገበው አትሌት ቀነኒሣ በቀለ ከ2002-2008 እ.ኤ.አ በተካሄዱት የዓለም ሻምፒዮናዎች ነው። ሌሎቹን 4 የወርቅ ሜዳልያዎች ደግሞ መሃመድ ከድር (በ1982 እ.ኤ.አ)፣ በቀለ ደበሌ (በ1983 እ.ኤ.አ)፣ ገብረእግዚአብሔር ገ/ማርያም (በ2009 እ.ኤ.አ) እንዲሁም ኢማና መርጋ በ2011 እ.ኤ.አ ላይ አስመዝግበዋል፡፡
በአዋቂ ሴቶች የ8 ኪ.ሜ የረጅም ርቀት ውድድር ደግሞ በኢትዮጵያዊ አትሌት የመጀመሪያ የሜዳልያ የተገኘው በ1991 እ.ኤ.አ ደራርቱ ቱሉ በወሰደችው የብር ሜዳልያ ነው፡፡ የመጀመሪያውን የወርቅ ሜዳሊያ ደግሞ በ1995 እ.ኤ.አ ላይ አሁንም ደራርቱ ቱሉ የተጐናፀፈች ሲሆን ሌሎች ሁለት የወርቅ ሜዳልያዎችን ደግሞ በ1975 እና በ2000 እ.ኤ.አ አግኝታለች፡፡ በአዋቂ ሴቶች ኢትዮጵያ ካስመዘገበቻቸው 9 የወርቅ ሜዳልያዎች 3 ከጥሩነሽ ዲባባ (በ2005፣በ2006፣ በ2008 እ.ኤ.አ) 2 በጌጤ ዋሚ (በ1996፣ በ1999 እ.ኤ.አ) እንዲሁም በወርቅነሽ ኪዳኔ (2003 እ.ኤ.አ) ተገኝተዋል፡፡
በርካታ የዓለም አገር አቋራጭ ሻምፒዮና ሜዳሊያዎችን በግል እና ከቡድን ጋር በማግኘት በወንዶች ቀነኒሳ በቀለ በአጠቃላይ 27 ሜዳሊያዎችን በመውሰድ ከዓለም አንደኛ ደረጃ ላይ ሲገኝ፣ በሴቶች ደግሞ ኢትዮጵያዊቷ ወርቅነሽ ኪዳኔ በ21 ሜዳሊያዎች መሪነቱ ላይ ተቀምጣለች። በግልና በቡድን የወርቅ ሜዳሊያዎች ድምር የአለም አገር አቋራጭን የተቆጣጠሩትም ኢትዮጵያዊያን አትሌቶች ናቸው። በወንዶች በግል ያገኛቸውን 12 ወርቅ ሜዳሊያዎች እና በቡድን ያገኛቸውን አራት የወርቅ ሜዳሊያዎች ጨምሮ በ16 ወርቅ ሜዳሊያዎች ቀነኒሳ በቀለ መሪነቱን ሲይዝ፣ በሴቶችም በግሏ አምስት፣ በቡድን ዘጠኝ የወርቅ ሜዳሊያዎችን ያገኘችው ጥሩነሽ ዲባባ በ14 ወርቅ ሜዳሊያዎች በሴቶቹ ምድብ  አንደኛነቱን ይዛለች። በዓለም አገር አቋራጭ ሻምፒዮና የተሳትፎ ታሪካቸው ቢያንስ አራት ሜዳሊያዎችን በማግኘት ሰባት የኢትዮጵያ አትሌቶች ክብረወሰኑ አላቸው። እነሱም ሀይሉ መኮንን፣ ጌጤ ዋሚ፣ ቀነኒሳ በቀለ፣ ወርቅነሽ ኪዳኔ፣ ገብረእግዚአብሄር ገብረማሪያም፣ ጥሩነሽ ዲባባ እና መሰለች መልካሙ ናቸው።

 አይኮግ ላብስ የተባለውና በወጣቶች የተቋቋመው የሶፍትዌር አማካሪ ድርጅቶች ከሳይንስና ቴክኖሎጂ ሚኒስትሮች ጋር በመተባበር፣ ዛሬ ከቀኑ 8 ሰዓት ጀምሮ በሳይንስና ቴክኖሎጂ ግቢ ውስጥ በመቀሌና በአራት ኪሎ ሳይንስ ፋኩልቲ ዩኒቨርስቲዎች መካከል የሮቦቶች የእግር ኳስ ውድድር ያካሂዳል፡፡ ድርጅቱ ባለፉት አምስት አመታት በአርቲፊሻል ኢንተለጀንስና በሮቦቲክስ ቢዝነስ ላይ ሲሰራ መቆየቱን ሰሞኑን በሳይንስና ቴክኖሎጂ ሚኒስቴር አዳራሽ በሰጠው ጋዜጣዊ መግለጫ አስታውቋል፡፡
ድርጅቱ የሚሰራው የአርቴፊሻል ኢንተለጀንስና የሮቦቲክስ ቢዝነስ በአገራችንም ሆነ በአፍሪካ ያልተደፈረ ስራ በመሆኑ ከውጭ ድርጅቶች ጋር ሲሰራ እንደነበር አስታውሶ፣ ነገር ግን ቢዝነሱ በአገር ውስጥ መተግበር ቢጀምር ችግር ፈቺ ይሆናል በሚል ሃሳብ ያለፈውን አንድ አመት ከ22 የአገራችን ዩኒቨርስቲዎች ጋር በጋራ ለመስራት ስምምነት መፈራረሙን የአይኮግ ላብስ መስራቾች ተናግረዋል፡፡
ሳይንሱን ከጨዋታና ከመዝናናት ለመጀመር ከዩኒቨርስቲው የተውጣጡ ሁለት ሁለት ተማሪዎች መርጦ ስልጠና ሲሰጥ የቆየ ሲሆን ተማሪዎቹ ውድድሩን በሮቦቶች ለማድረግ፣ ሮቦቶቹን ከመገጣጠም ጀምሮ ወደ ተቃራኒ ጎል እንዴት መምታት እንዳለበት፣ እንዴት ጎል ማስገባትና ኳስ ለቡድኑ ተጫዋች ማቀበል እንደሚችል ----- ሮቦቶቹን ፕሮግራም በማድረግ አዘጋጅተዋል ተብሏል፡፡ ለፍፃሜ ውድድር ያለፉት መቀሌ ዩኒቨርስቲና በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ አራት ኪሎ ፋኩልቲ እንደሆኑ በመግለጫው ላይ ተጠቁሟል፡፡  
የሳይንስና ቴክኖሎጂ ሚኒስቴር ሚኒስትር ዴኤታ ፕሮፌሰር አፈወርቅ ካሱ፤”ወጣቶቹ በአገራችን ብቸኛ የአርቴፊሻል ኢንተለጀንስና የሮቦቲክ ቢዝነስ ፈጣሪዎች ናቸው፡፡ ስለዚህም ለሥራቸው ከፍተኛ እውቅና በመስጠት ከሚኒስቴሩ ጋር በጋራ እንዲሰሩ አድርገናል” ብለዋል፡፡ ሚኒስቴር መስሪያ ቤቱ ለፈጠራ ስራ ከፍተኛ ቦታ በመስጠት የፈጠራ ባለሙያዎችን  ለማበረታታት በየዓመቱ ሽልማት እንደሚሰጥ ጠቅሰው፣ ዘንድሮም ለሰባተኛ ጊዜ ይህ ሽልማት ለፈጠራ ባለሙያዎች መሰጠቱን ገልፀዋል፡፡
አይኮግ ለመጀመሪያ ጊዜ የሚያካሂደው ‹‹አይኮግ ሜከርስ ሮቦ ሶከር ካፕ›› በየአመቱ ቀጣይነት እንደሚኖረው ለማወቅ ተችሏል፡፡ የሮቦት እግር ኳስ ውድድሩን ለመጫወት 3 ሜ. በ 2 ሜ የሆነ ሜዳና ከእያንዳንዱ ቡድን ሶስት ሶስት ሮቦት እንደሚያስፈልጉ የተገለጸ ሲሆን ለአሸናፊው ቡድን ከሳይንስና ቴክኖሎጂ ሚኒስቴር ሽልማት ይበረከታል ተብሏል፡፡

 “--አሁን አሁን በፈረንጆች ብቻ ሳይሆን በኢትዮጵያዊያን ወጣቶች ጭምር ስትዘወተር የምንሰማት            አንድ ጥያቄ አለች፡ “ሁሉን ነገር እኛ ጀመርነው ልትሉ ነው?” ሁሉን ነገር ባይሆንም አብዛኛው ነገር ሲጀመር፣          እኛም ከጀማሪዎቹ መካከል መሆናችንን የሚያስረዳ ረጅም ታሪካችንን “ደብተራ የጻፈው” እያሉ ማጣጣል           የምሁርነት ወፌ ቆመች ሆኗል፡፡---”
                       ሙሉጌታ አለባቸው

     (ካለፈው የቀጠለ)
ማርቆስ ረታ እና አዳም ረታ
“የስንብት ቀለማት”ን አንብቤ ስጨርስ ከጥቂት ዓመታት በፊት ያነበብኩት አንድ መጽሐፍ ትዝ አለኝ፡፡ መጽሐፉ በማርቆስ ረታ የተጻፈ ሲሆን ርዕሱ፡- “Organic Ethiopia: Reflections on its search, confusion and way-out” ይላል፡፡ ከርዕሱ እንደምንረዳው አዳም በልቦለድ ያሳየውን ማርቆስ በኢ-ልቦለድ ለማቅረብ ሞክሯል፡፡ ማርቆስና አዳም በብዙ ነገር ይመሳሰላሉ፡፡ (የአባታቸው ስም አንድ መሆኑ ግን ተራ አጋጣሚ ነው)፡፡
በጠቅላላው የሚያመሳስላቸው ሁለቱም አገር አቀፍ ችግር ውስጥ መሆናችንን ማመናቸው፣ የችግሩን ምንጭ ለመመርመር መሞከራቸውና መፍትሄ ለማመላከት ጥረት ማድረጋቸው ነው፡፡ ሁለቱን ማነጻጸር ሰፊ ጥናትን የሚጋብዝ ቢሆንም ለአሁኑ ግን በቀላሉ ከሚታዩ አንድነታቸው መካከል ምሳሌዎች እያነሳሁ ለማየት ልሞክር፡፡ የመጀመሪያው ተመሳስሎ መንግሥታዊ ያልሆኑ ድርጅቶች ጉዳይ ነው፡፡ መያዶች በሁለቱም መጽሐፎች በሰፊው ተነቅፈዋል፡፡ የገንዘብ አቅማቸውን ተመክተው ኢትዮጵያዊ አስተሳሰቦችን በመጨቆን፣ የራሳቸውን እምነትና ባሕል ለመጫን የሚሞክሩ የምዕራብ መሣሪያዎች ሆነው ቀርበዋል፡፡
“the once independent and proud citizens [Ethiopians] are being taught to look up to the same people – who have come to make a living out of the disaster they [NGOs] exaggerate and magnify through their subtle art of censoring our activities by offering and/or refusing sponsorship.”
ማርቆስ ይሄን የመያዶችን የ“ማሰልጠን” ተልዕኮ ሲተች፤ እነሱ ኋላ ቀር የሚሉት ጎጂ ልማድ በባሕላችን ግን ተወዳጅ እሴት ሊሆን እንደሚችል ለማስረዳት በአስራ ስድስት አመቷ የሃምሳ አመት ሰው ያገባች አክስቱን ምሳሌ ያመጣል፡፡ “…ሁለት ወንድና አንድ ሴት ልጅ ወልደዋል፡፡ በሙያ ዳኛ የነበረው ባለቤቷ ወደ ፍርድ ቤት ለሥራ ሲሄድ በጣም ቆንጆ ከመሆኗ የተነሳ ቤት ውስጥ ቆልፎባት ይሄድ እንደነበር ነግራኛለች፡፡ ይሄን እያስታወሰች ስትነግረኝ ፊቷ ላይ የማየው ፈገግታ እንጂ ሐዘን አለመሆኑ ያስገርማል፡፡ በዚህ የባሏ ድርጊት ውስጥ ለእሷ የሚታያት ቀናተኛ አፍቃሪ እንጂ ጨቋኝ ባል ስላልሆነ ደስ ተሰኘች (she felt flattered)!” ይላል፡፡ በስንብት ቀለማት ደግሞ ፊያሜታ የምታስተዳድረው ሴሕጤድ የሚባል አስቂኝ ስም ያለው መያድ፤ የሴቶች ግርዛትን የማስቆም አጀንዳ ይዞ ይሠራል፡፡ ፊያሜታ ለረጅም ጊዜ ውጪ አገር ቆይታ የመጣች ሴት ስለሆነች “ሰልጥናለች” (ገንዘብ የለኝም ለማለት “አምስት ሣንቲ የለኝም” ስትል ግን ሆን ብላ የድሮውን ብትረሳም ያደገችበትን ፍቃ ማጥፋት እንደሚሳናት ታጋልጣለች)፡፡ የልጅነት አፍቃሪዋ ሚኒሊክ ባዩ፣ አገር ቤት መምጣቷን ሰምቶ፣ ሰላምታ ሊያቀርብላት ሴቶችን ሰብስባ ስልጠና የምትሰጥበት ቦታ ድረስ ይሄዳል፡፡ አላውቅህም ብላ መካዷ ሳያንስ ከሩቅ ቆሞ እስክትጨርስ የሚጠብቃትን ሚኒሊክ፣ የፈረንጅ ሀሳብ ተውሳ “አይገርምም? ቬሪ ስትሬንጅ ዚስ ኢዝ ስቶኪንግ” ትላለች፡፡ ተራኪው ይቀጥላል… “ከአሜሪካ ለቃቅማ ያመጣቻትን ዝባዝንኬ ፅንሰ-ሀሳብ  እዚህ አገር ላይ ስትለጥፍብን፡፡ “ስትሄድ ስከተላት” የተባለ ዘፈን አልሰማችም? የሐበሻ ሴት ስቶክ ተደርጋ እንደምትበላ፤ ስቶክ ካላደረጓት ያልፈለጓት እንደሚመስላት አታውቅም? ረሳች?”
ሁለቱ ጸሐፍት የሚመሳሰሉበት ሌላው ነጥብ ምሁሩንና አርቲስቱን የሚተቹበት መንገድ ነው፡፡ ለማርቆስ ያለንን ነገርና የጎደለንን ነገር ለይቶ ማሳየት የሚገባው አርቲስቱ ነው፡፡ “the crux of most of our confusion is our ignorance of what we have and what we have yet to seek, as well as the widespread cluelessness of Ethiopian virtues we have to retain” ካለ በኋላ ይሄንን ባለማድረጋቸው አርቲስቶቻችንን ይወቅሳል። አርቲስቶቻችን ታሪክና ቅርሳችንን የሚያጎላ፤ በአገራችን እንድንኮራ የሚያደርገን የጥበብ ስራ ከመሥራት ይልቅ ቀለብ የሚሰፍሩላቸው መያዶች (ምዕራባዊያን) ያስቀመጡትን አጀንዳ ለማሳካት ይለፋሉ ይላል፡፡ አዳም ደግሞ ምሁራኖቻችንን እንደዚህ ይተቻል፡- “የኢትዮጵያ ምሁራን ሲሰለጥኑና ዘሮቻቸውን ሊያሰለጥኑ ሲፈልጉ መጽሐፎች ይጽፋሉ፡፡ በነዚህ መፅሐፎች ውስጥ የሚጠይቁት አንድ ዋነኛ ጥያቄ እኔ ምን አለኝ? ሳይሆን እነሱ ምን አላቸው? ነው አሉ፡፡…ካላመናችሁ ጃፓን እንደምን ሰለጠነችን ያንብቡ… ”
የሁለቱ “ረታዎች” ተመሳስሎ ለማሳየት ከምሞክረው በላይ አስገራሚ ነው፡፡ አንዳንድ ነጥቦች ላይ ተመሳስሏቸው ቃል በቃል ወደሚመስል ደረጃ ይጠጋል፡፡ በሀሳብ ደረጃ ደግሞ አገራችን አሁን ለገባችበት አዘቅት ዋና ተጠያቂ ከሚያደርጉት አካል አንዱ፣ያ ትውልድ ነው፡፡ ለራሱ “ያ ትውልድ” የሚል መጠሪያ ያወጣው ትውልድ አባላት፤“ሁሉም ያለ ምህረት፣ ያለ በቂ ትንታኔ የዛሬውን ወጣት ያማሉ፡፡ … ወጣት ድሮ ቀረ አንዱ ወሬያቸው ነው፡፡ ድሮ ሲሉ እኛ ማለታቸው ነው” ይላል - “የስንብት ቀለማት”። Organic Ethiopia ደግሞ፡- “Whenever they make comparisons, they are likely to assert that the good old days, their days, were far more productive, the real times of the flourishing Ethiopian art [and by extension everything else!]” ይለናል፡፡
አዳምና ማርቆስን በሁለቱ መጻሕፍት እንመዝናቸው ብንል፣ ሁለቱም አገራቸውን የሚወዱ ብሔረተኞች እንደሆኑ መገመት የተለየ ጥበብ አይጠይቅም፡፡ ምዕራባዊያንን አስመልክቶ nearly xenophobic የሆነ አመለካከት አላቸው ለማለት ደግሞ የሁለቱን መጽሐፍት ይዘት መረዳት ብቻ ይበቃል፡፡ በስንብት ቀለማትም ሆነ በOrganic Ethiopia “ባዴ” (ባእድ ከሚለው የመጣ የአዳም ቃል) አይበጀንም፡፡  አስፈላጊነቱን ሳንመረምር የምናስገባው የባዴ ሀሳብና ቁስ ግን ልዩ ክብር ይሰጠዋል፡፡ አገር በቀል ከሆነ ተመሳሳይ ሀሳብና ቁስ ጋር ሲወዳደር የባእዱ ይሰገድለታል፡፡ ለዚህ አንዱ ማስረጃ “ከውጭ የመጣ ነው” በሚል አረፍተ ነገር ታጅቦ የሚቀርብ ማንኛውም ነገር የሚታይበት መንገድ ነው፡፡ አዲስ አሠራር፣ መድሃኒት፣ ልብስ፣ ስልጠና ወዘተ “ከውጭ የመጣ” ከተባለ ሌላ ተጨማሪ ጥያቄ ሳይቀርብ ምርጥነቱ ይረጋገጣል። “ከሌላ ፕላኔት” እንደመጣ ሁሉ እንደ ተአምር ይታያል፡፡ በአዳም መጽሐፍ ውስጥ የሚገኘው ዘ ድሬክ የተባለ ሆቴል (ስሙ እንኳ ከውጭ የመጣ!) “…የተገነባባቸው እቃዎች ከድንጋዩ በስተቀር ሁሉም ከውጭ የመጡ ናቸው፡፡ ከውጭ ሀገር አይደለም። ከውጭ (ለብቻው ቃሉ ሲባል ሌላ ፕላኔትም ይመስላል)…” በማርቆስ መጽሐፍ ተመሳሳይ ሀሳብ በሌላ አገላለጽ እንዲህ ተቀምጧል፡-
“The operative parameter already established as an unquestionable truth is that whatever domestic is bad/ inferior and whatever comes from overseas good superior. Not just in goods, but in everything; the Ethiopian way of doing things is considered to be inferior, uncivilized.”
በመጨረሻም ሁለቱ መጽሐፍት/ጸሐፊያን አገራችንን ከገባችበት ችግር ለማውጣት የሚያስቀምጡትን የመፍትሔ ሀሳብ አንስቼ ወደ ቀጣዩ ርዕስ ልሂድ፡፡
“Let’s drop all ‘-isms’… they blind most of us from seeing what really concerns us” የሚለው ማርቆስ፤ ያለንና የሌለንን ከለየን በኋላ የራሳችን የምንለው አገር በቀል የሆነ “ኢዝም”፤ አዲስ ሕልዮ ማፍለቅ ይቻለን ይሆናል ይላል፡፡ “…we may even come across with the notion of coining our own – home grown –ism.”
ይሄ ደግሞ በስንብት ቀለማት የተነሳው አብይ ጭብጥ ነው፡፡ “ተረት ይመስላል” በሚለው የመጨረሻው ምዕራፍ፤ ምትኬ በተባለች ልጃገረድና መንኮብያ በተባለ ልዕለ ሰብዕ (እርሱም የማንነታችን ሁሉ ወኪል የሆነ) ተራክቦ፣ የሰው ስጋ ለብሶ የሚወለድ ማኩታ፤ የራሳችን የምንለው አዲስ ሀሳብ አዲስ ማንነት ይወለዳልና!
ማንነት ምንድን ነው?
“…የመቃረን አለም ውስጥ እንዳለ ያውቃል፡፡ ወደ ኋላ መመለስ ʻማንነትʼ ከሆነ፤ ፒሳ ሳይሆን ማንነቱ ቂጣ ነው፤ ያውም ያረረ፡፡ ሀምበርገር አይደለም ማንነቱ፤ ጣቶቹ ላይ እየፈረሰ የሚያስቸግረው ዘንጋዳ እንጀራ ነው፡፡ ማንነት ከተባለ የሚለብሰው የካልቪን ክላይን ውስጥ ሱሪ አይደለም፤ በጠጡና ጉድፍ ሬንጅ ያስመሰላት ቁምጣው ወይ ንፍጡ ያጠቆራት ጥብቆ ናት፡፡ ብዙ ሳያስብ ያውቃል፤ ማንነቱ በየጎጆ ቤቱ በወባ ትንኝ ከነዘር ማንዘሩ መዘረር ነው። ማንነቱ ወደ ኋላ እየተገፋ ዝንጀሮ ጋ ባይደርስ እንኳን በልጅነቱ ቀን ከቀን በየሜዳው የነሰነሰው ኮሌራው ነው፡፡ ዘፈኑ ሮክ ኤንድ ሮል ሳይሆን ሆዱ በወስፋት ሲጮህ ነው፡፡ ማንነቱ ከአፍንጫው ላይ በእጁ ሲያባርር የገደላቸው የትንኝ ሞሳዎች ናቸው። ማንነቱ ሄኒኬን ቢራ ማንቃረር ሳይሆን በእንትን እንኩሮ የጠየመ አሰር ትፍ ማለት ነው፡፡ ማንነቱ መንገድ ዳር ቁጢጥ ብሎ ለበቆሎ ጠባሽ የተናገራት ‹ያቺኛዋን ስጠኝ› ዐማርኛ ናት፡፡ ማንነቱ በጥፍር የነገለ አውራ ጣቱን በቆሻሻ ጨርቅ መተኮስ ነው። አሸናፊ ባያወራውም፡፡ እነ ዶክተር ባያወሩትም። አናፍርበትም ብለው ግን ሌላ ሌላ ቢዘባርቁም……”
ከላይ የቀረበው ገለጻ በልቦለዱ ውስጥ የሚገኘው አሸናፊ የተባለ ሰው ማንነት ነው፡፡ አሸናፊ ግን ይሄን በአደባባይ ይክደዋል፡፡ ልክ እንደ አሸናፊ ሁሉ ብዙ ኢትዮጵያዊ የመቃረን ዓለም ውስጥ ነው፡፡ ፈረንጅ ለመምሰል ይለፋል፤ ግን እውነተኛ ማንነቱን የሚደብቅባት ትንሽ ልቡ እሺ አትለውም፡፡  በቅርብ ዘመን የተራቆተ ኪሱን እየጠቆሙ “ማንነት የለህም” ሲሉት የሚለግሱት ስንዴና ዘይት እንዳይቀርበት “አዎ የለኝም” ብሎ ምንም ይሆናል፡፡ ማንነቱ አባቶቹ በማለዳ መሠልጠናቸው፤ የዓለምን እውቀትና ምስጢር የተረዱ መሆናቸው መሆኑን ዘንግቷል (እንዲዘነጋ ተደርጓል)፡፡
አሁን አሁን በፈረንጆች ብቻ ሳይሆን በኢትዮጵያዊያን ወጣቶች ጭምር ስትዘወተር የምንሰማት አንድ ጥያቄ አለች፡ “ሁሉን ነገር እኛ ጀመርነው ልትሉ ነው?” ሁሉን ነገር ባይሆንም አብዛኛው ነገር ሲጀመር፣ እኛም ከጀማሪዎቹ መካከል መሆናችንን የሚያስረዳ ረጅም ታሪካችንን “ደብተራ የጻፈው” እያሉ ማጣጣል የምሁርነት ወፌ ቆመች ሆኗል፡፡ እና ደብተራ የጻፈው እንደሆነስ? “የማንም አገር ታሪክ የተጻፈው በደብተራ ነው” (የስንብት ቀለማት)። ጅምር ምሁሬ ሆይ! የፈረንጅ ደብተራ የለውም መሰለህ? አለው! የማርቆስ ረታን አባባል ልጠቀምና እንዲህ “ክፍ” ልበላችሁ… Get off mom’s back!
«የስንብት ቀለማት» እንዲህ ይላል… “[ፈረንጆች] የእኛን አንድ የአራዳውን ፈረሰኛ ግን እንድንጠላ ይገፋፉናል፣ እምቢ ስንል ደሞ ያጣጥሉታል፣ ማጣጣላቸው አልገባን ካለ በዓለም ያስቁብናል፣ ሳቂ ካጡ ታሪካችንን ይዘርፉናል፣ እሱም የእኛ ነው ብለን ከተሟዘዝን በተለይ ጥቋቁር ሽርኮቻቸውን (ሀበፈረንጃውያንን) ሰብስበው ወደ እኛ እየጠቆሙ የበለጠ ያስቁብናል፡፡ እንዲህም ይነዘንዙናል፡፡ አሁንስ በዛ (ባይበዛም) ሁሉን ነገር እኛ ጀመርነው ልትሉ ነው? (አልወጣንም)፡፡”
ቆይ ሁሉን ነገር ጀመርነው ብንልስ? ራሳቸው ያመጡትን ሳይንስ ምስክር ጠርተን የሰው ዘር የጀመረው እዚች አገር ላይ ነው ብንልስ? የሰጡንን መጽሐፍ ቅዱስ ጠቅሰን አዳምና ሄዋን የኖሩት ኢትዮጵያ ነበር ብንልስ?
የመጣንበትን ግን ስለዘነጋነው የራሳችን ነው የምንለው ነገር እንዳልነበረን፣ ድርጊታችን ሁሉ በመቅዳት ላይ ተመስርቷል፡፡ ይሄን ምክንያታዊ አድርገን ለማስረዳት የምንጠቀመው አባባል ደሞ “ፈረንጆችኮ…” ብሎ የሚጀምር ፉርሽ ማነጻጸሪያ ነው፡፡ «የስንብት ቀለማት» ከውጪ አገር ስንወስድ ቢያንስ ወደ ራሳችን ሁኔታ እንዲስማማ እያደረግን መውሰድ እንዳለብን ለማስረዳት ፌብሩወሪ አስራ አራት የሚከበረውን ʻቫለንታይንስ ዴይʼ በአደይ ቀን ተክቷል፡፡ የበአሉ መገለጫ የሆነውን ቀይ ቀለምና ቀይ አበባ እኛን ወደሚገልጸው ቢጫ ቀለምና አደይ አበባ መልሷል፡፡
ሐበሻ (ሌሎች እሱን ለመስደብ ያወጡለትን ስም እንደ ምርቃት ቆጥሮ በኩራት ራሱን በዚህ ስም የሚጠራ አስገራሚ ሕዝብ) ሲቀዳ ሙልጭ አድርጎ ነው፡፡ አንድን ጸጉረ ልውጥ ሀሳብ ሲቀበል ከእነ እርግማኑ ነው፡፡ “ለወንድሞችህ የባሪያዎች ባሪያ ሁን” የሚል እርግማን በግልጽ የተጻፈባቸውን ቅዱሳን መጻሕፍት እንኳን አሜን ብሎ ተቀብሎ “ይንጀላጀላል”፡፡ ሳላይሽ እንዲህ ታብራራዋለች፡- “የምቀኝነቴ ትክክለኛነት የሚታወቀኝ አንዱ የካም መረገም ታሪክ ነው፡፡ ሁሉም ከኦርቶዶክስ እስከ ጴንጤ ያለ ሐበሻ የተሰደበበትን ቅዱስ መጽሐፍ ተሸክሞ ይንጀላጀላል፡፡ በውዳቂ ታሪክ የእናቱን ጡት ሳይጠግብ ከቄስ፣ ከክርስትና አባትና ከድፎ ዳቦ ጋር ተባብሮ ራሱን ይገድላል፡፡ እኔ ማሳበቢያ ሆንኩ እንጂ ሲፈጠር የተሰጠውን እርግማን ነው እንዳይረሳው የምሰጠው፡፡ ክርስቲያን ሐበሻ፣ እስላም ሐበሻ ሆይ፤ የካም እርግማንን አስብ፣ ለደይን ተመርጠሃል እላለሁ”
ለደይን የተመረጥንባቸውን መጻሕፍት እየገለጥንም ለልጆቻችን የአይሁድ ስም ማውጣት ልማድ ሆኗል። ምክንያታችን ሃይማኖታችንን መውደዳችን ወይስ የዝቅተኛነት ስሜት? «የስንብት ቀለማት» ይሄንንም ይጠይቃል፡፡ “ለምንድን ነው የዚህ አገር ሰው ልሳን እንደሌለው ሁሉ ለወለደው ልጁ ብቻ ሳይሆን ለውሻውም ስም ልመና ቁናውን ይዞ መካከለኛው ምሥራቅ የሚሄደው? ሃይማኖቱን ስለሚወድ ነው ወይስ ዝቅተኛነትን ስለሚወድ?” መጠሪያ ስም ማንነት ነው፡፡ ወላጆች ለልጆቻቸው ስያሜ ሲሰጡ እምነትና ተስፋቸውን እያስቀመጡ ነው፡፡ ማሕበረሰብ ልጆቹን ሲሰይም ማንነት ፍለጋ ባሕር ተሻግሮ ከሄደ ጤና ማጣቱን ሊያመላክት ይችላል፡፡ “…ለስም ለስምማ ዮሴፍ የይሁዳውያን ነው፡፡ ታዲያ ማንነቴን ለማግኘት እየሩሳሌም መሄድ አለብኝ?” ይላል ዶክተር ዮሴፍ፡፡ «ማሕሌት» ከተሰኘው የደራሲው የበኩር ሥራ ተጠልፋ «የስንበት ቀለማት» ውስጥ የተገኘችው ኤልዛቤልም ሌላ ምሳሌ መሆን ትችላለች፡፡ “ሰላማዊት”ን የመሰለ ሰላማዊ ስም እያላት በአመንዝራ ሴት ስም የምትጠራበት ኤልዛቤል የተባለ ስሟ መመረጡ በራሳችን ቋንቋ ከሚመርቁን፣ በባዕድ አፍ ቢረግሙን እንደምንመርጥ ያሳያል፡፡
«የስንብት ቀለማት» ለዚህ መፍትሔ የሚጠቁም ልቦለድ ነው፡፡ (ልቦለድ ስለው ቅር ይለኛል!) መፍትሔው ወደ ውስጣችን መመልከት ነው፡፡ እንደ ዮሐንስ ወላይሶ የራሳችንን ዐይኖች ማየት፡፡ ወይም ወደ ራሳችን መመልከት፡፡ እንደ እኔ እምነት፤ የመጽሐፉ ደራሲ ወደ ራሱ ተመልክቷል፡፡ የራሱን ዐይኖች አይቶ ያገኘው ደግሞ እስካሁን የሰጠንን መጽሐፍቱን ብቻ ሳይሆን “ሕጽናዊነት” የተባለ የአጻጻፍ ስልቱንም ነው፡፡
ሕጽናዊነት በስንብት ቀለማት
ደራሲው እንጀራ ላይ ተመስርቶ የፈጠረውን ሕጽናዊነት የተባለ የአጻጻፍ ስልት ለማዳበር በታሪክ መንገድ ወደ ኋላ ተጉዞ፣ ከክርስቶስ ልደት በፊት 1500 ዓመት ላይ ያርፋል፡፡ ይህ ጊዜ ኢትኤል የተሰኘ ንጉሥ ገዢ የነበረበትና ለመጀመሪያ ጊዜ የጤፍ እንጀራ የተጋገረበት ዘመን ነው፡፡ “ጥንታዊያኑ ሰዎች በምግቦቻችንንና አመጋገባችን ጨምሮ በእያንዳንዱ ድርጊት ውስጥ ምስጢር የማስቀመጥ ጠባይ እንዳላቸው ይገባኛል፡፡ እንጀራን ሲፈጥሩት፤ ያወረሱን ምግብን ብቻ አይደለም፡፡ በሙለኩለኤው፣ በአገራችንና በግለሰቦች መካከል ያለውን ግንኙነትም ጭምር እንጂ” ይላል ደራሲው፡፡
በቅርጽ ረገድ ሕጽናዊነት ከእንጀራ የቀዳው ዋና ጸባይ አንዱ፣ ታሪክ ከሌላው ታሪክ ጋር በቀጫጭን የትረካ መስመሮች መገናኘቱ ነው፡፡ የእንጀራ ዐይኖች ከላይ ስናያቸው ራሳቸውን ችለው የቆሙ ቢመስሉም ከስር ግን ይገናኛሉ፡፡ በሕጽናዊነት ሰዎችና ነገሮች የማይገናኙ ቢመስሉም እንደ ደሴት ብቻውን የሚቆም አካል የለም፡፡ በሚዘረጋው የግንኙነት መረብ ውስጥ ሁሉም ገጸ-ባሕሪ ከሌላው ጋር በሆነ ዐይነት የሚታወቅም ሆነ የማይታወቅ መንገድ አንዱ ከሌላው ይያያዛል፡፡ ከዚህ በተጨማሪ የሕጽናዊነት አንድ ንዑስ ገጽታ ተጨማሪ ታሪኮችን በሕዳግ ማስታወሻ መተረኩ ነው፡፡
ሕጽናዊነት የቅርጽና የይዘት ብልህ ውህደት ነው፡፡ አንዱ ያለ ሌላኛው መቆም አይችልም፡፡ ደራሲው በታሪክ መንገድ ላይ የኋሊት ተጉዞ እንጀራ ላይ ሲያርፍ፣ ጥረቱ አዲስ ቅርጽ የመፍጠር ብቻ አለመሆኑን ከድርሰቶቹ ይዘት ማየት ይቻላል፡፡ ሙሉ ሂደቱ ማንነትን  ፍለጋና ወደ ማንነት መመለስ ነው፡፡
ከዚህ አንጻር “የስንብት ቀለማት”ን ሳየው… I just love how meticulous and intricate the whole book is! ረቂቅና እንከን የለሽ የታሪክና የሀሳብ አወቃቀሩ አጀብ የሚያስብል ነው፡፡ ሕጽናዊነት ከዚህ በላይ ሊሻሻል አይችልም፡፡ ፍጽምና ደረጃ ላይ ደርሷል፡፡ የጎመራ ሕጽናዊነት ልበለው?
ደራሲው ከዚህ በፊት ሕዳግ ማስታወሻዎችን እንዴት በጥንቃቄ እንደሚያዋቅር ያየሁት “ከሰማይ የወረደ ፍርፍር” በተባለው መጽሐፉ ነው፡፡ በዚህ መጽሐፍ ውስጥ “ዱለት፣ ጎሬና ጎሮ” በተሰኘው ታሪክ፤“ስልጣኔ እና ምቀኝነት” የተባለ ምናባዊ ማጣቀሻ መጽሐፍ ይገኛል፡፡ በሰሌዳ ጎማ ወርቅ በተባሉ ጸሐፊ በ1900 ዓ.ም እንደተጻፈ የተነገረን ይሄው መጽሐፍ፣ የታተመው ሁመራ ማተሚያ ቤት እንደሆነም ተገልጾልናል፡፡ ዋናው ጉዳይ ሁመራ ማተሚያ ቤት መታተሙ ነው፡፡ ለምን ሁመራ? የዚህ መልስ በዚያው ታሪክ ውስጥ በሌላ የሕዳግ ማስታወሻ ተቀምጦልናል። ምክንያቱ “የመግለጥ ቅጣት” ነው፡፡ ቅጣቱ እንደ ሕገ የተደነገገው እንዲህ ነው፡ “አንድ ደራሲ በተወሰነ ጊዜ ውስጥ ከተወሰኑ ገጾች በላይ እንዲጽፍ አይፈለግም፡፡ ምክንያቱም ጥራት እንዳይወድቅ ነው ይባላል፡፡ ይሄን ለማበረታታት የቀለም ራሽን ተወስኗል፡፡ ይሄን ድንጋጌ የጣሰ ደራሲ እንደ ጥፋቱ መጠን መጽሐፍ እንዳያነብ ይከለከላል፡፡… ይህ ʻየመግለፅ ቅጣትʼ ይባላል፡፡ … ሳይገባቸው ወይም ሕጉን ሳይረዱት የነዚህን ደራሲያን ግጥሞች ያተሙ ማተሚያ ቤቶች ካሉበት ቦታ ተነቅለው በረሃ መሐል እንዲተከሉ ይደረጋል”
ሁመራ ማተሚያ ቤት የተባለውም ደራሲው/ዋ በሰሌዳ ጎማወርቅ የዚህ ቅጣት ሰለባ በመሆኑ/ኗ መጽሐፉ የታተመው ሕጉን ሳይረዳ የነዚህ ዐይነት ደራሲን መጽሐፍት ስለሚያትም ሁመራ በረሃ መሐል እንዲተከል በተደረገ ማተሚያ ቤት በመሆኑ ነው፡፡ በሕጽናዊነት ሆን ተብሎ እንጂ እንዲሁ የሚጨመር መረጃ አለመኖሩን ልብ ይሏል!
በስንብት ቀለማት ደግሞ በሕዳግ ማስታወሻ የተቀመጡት ብዙዎቹ ቀያይ መረጃዎች ደረቅ እውነቶች ናቸው፡፡ ሆኖም ከዋናው ትረካ ተገንጥለው የተቀመጡ አይደሉም፤ እንዲያውም በዋናው ትረካ ውስጥ በገጸ ባሕሪያቱ ንግግር ውስጥ እዚህና እዚያ ተበትነው እናገኛቸዋለን፡፡ ዮሐንስ ወላይሶ ስለ ስንዝሮ ኮምፕሌክስ እና ስለ ማሞ ኮምፕሌክስ በሕዳግ ማስታወሻ ላይ አስረድተውን ያልፋሉ፡፡ ሀሳቡ ግን ትረካው ውስጥ እነ ፊያሜታ ከእነ ዶክተር አሳምነውና ከእነ ዶክተር ዮሴፍ ጋር ያላቸው ግንኙነት ጠባይ ሆኖ ይመጣል፡፡ አቶ ዮሐንስ አሁንም በሕዳግ ማስታወሻ ስለ ሰዎች ድአ መለያየት (የአፍ እና የድርጊት መለያየት) ሲያነሱ ዋናው ትረካ ውስጥ ድአቸው የተለያየ ነው እንባላለን፡፡ “ለምን ይሆን ድርጊታቸውና አፋቸው የማይመሳሰለው? ለምንድን ድአቸው ከአንድ ፍጡር የመጣ አልመስል አለ? … ሰዎች በድርጊት እየቀረቡ በአፍ እንዴት ይርቃሉ? በአፍ እየቀረቡ እንዴት በድርጊት ይርቃሉ?…” በተጨማሪም አቶ ዮሐንስ ስለ ሃቅላዊያን በሰንጠረዥ ጭምር ካስረዱን በኋላ ምትኬ እንዲህ ትለናለች፡- “…ዕድሜ ልኬን የጎደለብኝ እኔ፡፡ የሃቅላዊያን ሊቀመንበር ነኝ…”
ሕጽናዊነት እንጀራ ላይ መመሥረቱን ያወደሱ እንደ ስንዱ/ሰነዱ ኬ. ገብረ ማሪያም አይነት ጸሐፍት፤ “እንጀራ የጋራ ስነ ልቦናችን ነው” ይላሉ። የደራሲው ሙከራም “እንጀራ በወል ልቦናችን ውስጥ የሚሰጠውን ሰፊ ቦታ ማሳየት መሆኑን እንጂ እንጀራን እንደ ስነ-ጽሑፋዊ ቅርጽ መጠቀም ብቻ አይደለም” ሲሉ ይመሰክራሉ፡፡ Adam’s experimentation with injera does not stop at the solid injera and its form. He also played with the place injera occupies in our collective psyche (so to speak)”. (An Ethiopian Life without Adam: 7-Kilo መጽሄት)
በዚህም ሕጽናዊነት የቅርጽ እና የይዘት ግሩም ውህደት ሆኗል፡፡ ቅርጹ ያለ ይዘቱ መቆም አይችልም። ይዘቱም እንደዛው፡፡ ደራሲው ታሪክን ሲቆፍር የአጻጻፍ ስልቱን ከማሻሻልም በላይ አገራዊ ማንነትን እያሰሰ እንደሆነ ከበርካታ መጻሕፍቱ እንረዳለን። ጠቅላላ ሂደቱም ወደዘነጋነው/እንድንዘነጋው ወደተደረገው ማንነታችን መመለስ ነው፡፡ በስንብት ቀለማት እንደታየው ደግሞ በዛሬ ዘመን ውስጥ ኢትዮጵያዊያን ሁሉ የሚያስጨንቁንን አገራዊ ችግሮች የሚያስወግድልን ምኞታዊ መፍትሄ  ማመላከት ነው፡፡
ሕጽናዊነትን የመሠረተው ከአገሪቷ ዕድሜ ጋር አቻ ሊሆን በሚችለው በእንጀራ ላይ መሆኑና አባቶቻችን የተዉልንን ምስጢራት ፈልፍሎ በማውጣት ላይ መጠመዱ አዳም ከተራ ደራሲነት በላይ መሆኑን ይጠቁማል፡፡ ለዚህ ነው «የስንብት ቀለማት» የአዲስ ርእይ፣ የአዲስ ርእዮትና የአዲስ አገር ምሥረታ መድበል ነው የተባለው፡፡ (ቴዎድሮስ ገብሬ፡ ድህረ ቃል)፡፡ ስንዱ ደግሞ “መረቅ ሁላችንንም የሚጠይቀን ታሪካችንን እንድናይና ነገ-አችንን አጥርተን እንድንስል ነው” ብላለች፡፡ ስንዱን በድጋሚ ለመጥቀስ “ለእኛ ለኢትዮጵያዊያን አዳም የሌለበት ሕይወት ማለት ትንሣዔ የሌለው ሕይወት ነው” ስትል ጽፋለች፡፡
“…የማይቀር ትንሣኤሽን ሳልም…”
ቢነጋም ባይነጋም
የተፈቀረ አይዘነጋም፡፡
ከመቶ ዓመት በፊት ተወልደሽ ከመቶ ዓመት በፊት ብትሞቺም
እንደ ጉም እኖራለሁ ሳልተኛ፣ የማይቀር ትንሣኤሽን ሳልም፡፡
ያልተፈጠረ ጉንጭሽን
እንደ ሰማያዊ ስጦታ ስስም፡፡
(ሰዓሊና ገጣሚ ወርቁ ዕንቁባሕሪ)
ኢትዮጵያ ለረጅም ዘመን የኖረችበት የሰሎሞናዊ ሥርዎ መንግሥትን አውታርና ካስማ ሆኖ ያቆመው የሰሎሞን-ሳባ-ምንይልክ ተረክ ነው፡፡ የ1953ቱን የንዋይ ወንድማማቾች የመፈንቅለ መንግሥት ሙከራ ተከትሎ የተነሳው የተማሪዎች ንቅናቄ ግን ይሄን ሚት ፈተና ውስጥ ከተተው፡፡ “ክፋቱ ንቅናቄው ፍጹም ከመጽሃፉ የተነሳ የየሰውን ልብ በአናርኪዝምና በኒሂሊዝም መንፈስ ሞላ፡፡ ማፍረስ ብቻ፤ መንቀል ብቻ ግቡ ሆነ፡፡ ነፍስ ያላወቀው [ያ]ትውልድ፣ በነቀለው እሴት ፋንታ አዲስ አልተከለም። ባለፈው ሮማንስ ምትክ ሌላ ሮማንስ አላበጀም፡፡ (ማርክሲዝምና ሌኒኒዝም አዲሱ ሮማንስ ነው ካላልን በቀር)” (ቴዎድሮስ ገብሬ፡ ድህረ ቃል)፡፡  
የንቅናቄው ፋና ወጊዎች እነ ዋለልኝ መኮንን “ብሔራዊ ቀሚስ ብሎ ነገር የለም” ባሉበት ጽሑፋቸው (1969)፤ኢትዮጵያዊ ብሔረተኝነት የሀሰት ነው ሲሉ ካዱ፡፡ “There is of course the fake Ethiopian Nationalism advanced by the ruling class and unwillingly accepted and even propagated by innocent fellow travellers”. ከዚያም ሰለሞናዊው ዙፋን ተሰበረ፡፡ ተረኩም ከአጼው መንግሥት ጋር ተቀበረ፡፡ በምትኩ ምን አመጡ? ሶሻሊስታዊ የእንጀራ አባቶቻቸውን እነ ሌኒንን እያጣቀሱ፤ “እውነተኛ nation state እንገንባ” አሉን፡፡ ይሄ እውነተኛ የተባለውስ ምንድር ነው ያልን እንደሆነ፤ It is a state in which all nationalities participate equally in state affairs, it is a state where every nationality is given equal opportunity to preserve and develop its language, its music and its history ይሉናል፡፡ ሁሉም ብሄረሰብ እየተነሳ ልገንጠል ቢልስ? ለሚለው ስጋታችን የሰጡን ምላሽ ደግሞ “ሶሻሊዝም’ኮ መጨረሻው አለም አቀፋዊነት ነው፤ ብንገነጣጠልም ተመልሰን አንድ እንሆናለን” የሚል ነበር፡፡ ይሄው ኤርትራ የራሷን ዕድል በራሷ ወስና ከተገነጠለች ሀያ አራት አመታት አለፉ፡፡ “ብንገነጣጠልም ተመልሰን አንድ እንሆናለን” ያሉን ተስፋ ግን ጉም እንደመዝገን ሆኖብናል፡፡
ዋለልኝ ስለ ዓለም አቀፋዊ ወንድማማችነት የሰበኩት ሶሻሊስት “ወንድሞቹ” በቆዳው ጥቁረት እየተሳለቁ በንቀት እንደሚያዩት ሳያውቅ ያለፈ “ነፍስ ያላወቀው ትውልድ” አባል ነበር፡፡ በማርቆስ ረታ አባባል፤ “አብዮታቸው አገራቸውንና ባሕሏን መረዳት ሳይሆን ስር ነቀል ለውጥ ማምጣትና ልክ እንደ ባእዳን አይነት ማድረግ ላይ ተጠምዶ ነበር” (Not to retain, not to comprehend the nation and its culture, but to change it, to do everything to make it look like the foreigners!) ሶሻሊዝም እና ዋለልኝ ሞተዋል፡፡ አገራችን ግን በዚያ ዘመን ጦስ ምክንያት ያለ ብሔራዊ ተረክ ቀርታለች፡፡ አገር አቀፍ ተረት አለመኖሩ ደግሞ አንድ ማህበረሰብ ትርጉም እንዲያጣ ያደርገዋል፡፡ “Myths are supposed to provide a dependable structure and sense of certainty, a firm foundation for a society’s sense of meaning.” (Mythic America)
አንድ አገር ያለ ብሔራዊ ተረክ፤ ያለ ሚት ቀረች ማለት አገሪቷ ነፍስ አልባ የመሆኗ ትእምርት ነው። በዚህ ዘመን ኢትዮጵያዊያን የተዘፈቅንበት የነፍስ ዝቅጠት፤ የባህል መጥፋት፤ የማንነት ቀውስና ሐሲር፣ ያለ ሚት የመቅረታችን መዘዝ ሊሆን ይችላል፡፡ (ቴዎድሮስ ገብሬ፡ ድህረ ቃል) ዛሬ በሃይማኖትና በዘር ተከፋፍለናል፡፡ ሁላችንንም የሚያግባባ፣ ሁላችንም በጋራ ልንቆምለት የምንችለው አንድም የወል ዓላማ የለንም፡፡ አገር ያለ ብሄራዊ ተረክ ቀርታለች፡፡
በሐሲር ጎዳና ሰከም ሰከም ከምትሉ የተማራችሁና ያልተማራችሁ ወገኖቼ መካከል ግን፤ እነሆ አዲስ አገራዊ ተረክ ለመፍጠር በነፍስ ወከፍ ተጋድሎ ያደረገ አንድ ደራሲ አገኘሁ፡፡ እውነት ግን በስንብት ቀለማት እንደሆነው ሁሉ “ነዋ በግዑ ለእግዚአብሔር፤ ዘየአትት ኃጢያተ ዓለም” ተብሎ የሚያድነን፤ ቤዛ ክሊኒክ ውስጥ የሚወለድ ማኩታ ይመጣልን ይሆን? ይፈጠርልን ይሆን ጠይም ክርስቶስ? “ዮም ተወለደ ቤዛ ኩሉ ዓለም” የሚል አምባር የሚያስርልን? ለአገራችን መድኃኒት የሆነ ዳግማዊ መልከ-ጸዴቅ ይወለድልን ይሆን?
እውነትም እንዲህ በመለኮታዊ ተዓምር ካልሆነ ከአገራዊ ዝቅጠታችን መውጣት የሚቻለን አይመስልም፡፡ ደራሲው ግን “There is no longer any religion of state… Religion has become something individual and concerns the conscience of each… it has nearly nothing to do with the reasons that determine the limits of various peoples” ከሚሉት ከእነ Ernest Renan ጋር የተስማማ ይመስላል፤ የሰሎሞን-ሳባ-ምንይልክን ተረክ የሚተካውን አዲሱን የስንዝሮ-ምትኬ-ማኩታ ሚት የሠራው ከሃይማኖት ነጻ አውጥቶ ነው፡፡ ወይም Edith Hamilton እውነተኛ ሚት ከሃይማኖት ጋር የሚያገናኘው ምንም ነገር የለም (A real myth has nothing to do with religion) ባለችው ይስማማል፡፡
ደራሲው ይሄን መስመር ለማስያዝ በውብ ቋንቋ ብዙ ደክሟል፡፡ “ይህ ሁሉ የኪነት ድካም አዲስ ብሔራዊ ምንነት የመገንባት፣ አዲስ አገር የመመስረት ጣጣ ነው፡፡ እናም ድርሰቱን እንደ ብሔርተኛ ሐቲት (as a national discourse) ልንቆጥረው እንችላለን” የሚለው ቴዎድሮስ ገብሬ፤ ለመሆኑ አንድ ደራሲ ስለ አገር ምሥረታ ምን አገባው? ሲል ይጠይቃል። መልሱም “ምን ጥያቄ አለው” የሚል ነው፡፡ ቴዎድሮስ አስተያየቱን ሲያጠቃልልም፤“እንዲያውም ዓበይት ከያኒያን--ሜጀር አርቲስት--የኪነታቸውና የተውሀቧቸው ዳርቻ ላይ መድረሳቸው የሚረጋገጠው በእንዲህ ያለው ተግባር መሆኑን ብዙዎች ይመሰክራሉ” ይላል፡፡
በ“እቴሜቴ ሎሚ ሽታ” ውስጥ ተነካነኪ የሚባል ጽንሰ ሀሳብ አለ፡፡ “በምትችለው መጠን ለአገርህ መልካም ነገር ለመሥራት መሳተፍ፡፡ አገርህን በተመለከተ ስለ ሁሉ ነገር ለማወቅ መጣር” ማለት ነው፡፡ “የስንብት ቀለማት” ደራሲ እንደ አንድ ብሔረተኛ ኢትዮጵያዊ እንዲሁም እንደ ደራሲ ማድረግ የሚገባውን ከፍ ባለ ደረጃ አድርጎታል፡፡ ሰብእናውና ደራሲነቱ ሲጨመቅ ዶፍ ሆኖ የወረደው “መረቅ” ደግሞ እነሆ የስንብት ቀለማት ነው፡፡ አዳም የለየለት ተነካናኪ ሆኗል፡፡
ከጥቂት ጊዜ በፊት ከአንድ የአዳም ክሪቲክ ጋር ስንጨዋወት ለምን እንደምንወደው ጠይቆኝ ነበር፡፡ ያኔ ገና “መረቅ” እንኳን አልወጣም ነበር፡፡ የመለስኩለት መልስ ግን “የስንብት ቀለማት”ን ካነበብኩ በኋላ ይመስላል፡፡ ደራሲው ምን ሊሠራ እንደሚችል ቀድመን ገምተናል መሰለኝ (አንባቢዎቹ ነቢይ ሳንሆን አንቀርም) “አዳምን የምወደው የገባንበትን አገር አቀፍ ችግር ከስሩ መርምሮ ምንጩን ስለሚጠቁመኝ፤ መውጫውንም ስለሚያመላክተኝ ነው…” አልኩ፡፡ ይሄ እውነተኛ ፍፃሜውን ያገኘው አሁን ነው፡፡
አዳም የኢትዮጵያን ልብ በፊደል ሥሎ እንካችሁ ብሏል፡፡ የቋንቋ አጠቃቀሙ “በአገርኛ ቋንቋም እንደዚህ መጻፍ ይቻላል እንዴ?” የሚያስብል ነው፡፡ ዐማርኛን ሰልጥኖባታል! ድርሰቱ በርካታ የእውቀት ዘርፎች በተራቀቀ ስልት ጥቅም ላይ ውለው በልዩ ኪናዊ አቀራረብ ተቀርፀውበታል፡፡ ኢትዮጵያና ኢትዮጵያዊነትን በተለየ መንገድ እንድናይ ያደርገናል። “የስንብት ቀለማት” ልቦለድ ብቻ ሳይሆን፤ ደራሲው የአገራችንን “የማይቀር ትንሣዔ” ያለመበት ታላቅ አገራዊ የኪነት፣ የእውነትና የእውቀት ሰነድ ነው፡፡ ይሄም ስለ መጽሐፉ ሊባልለት ከሚችለው ሲሶውን እንኳን አይሆንም፡፡

 በደራሲ አብይ ፈቅ ይበሉ የተፃፈው ‹‹ኪሩቤል›› የተሰኘ ረጅም ልብወለድ መፅሀፍ ዛሬ ከቀኑ 10፡00 ጀምሮ በደብረዳሞ ሆቴል እንደሚመረቅ የፕሮግራሙ አዘጋጅ አብይ ኢንተርናሽናል ፊልም ፕሮዳክሽን አስታወቀ፡፡
  በፍቅር፣ በታማኝነት፣ በዓላማ ፅናትና በተንኮል ዙሪያ የሚያጠነጥነው መፅሀፉ፤ በ300 ገፆች ተመጥኖ ለአገር ውስጥ በ79 ብር ከ50 ሣንቲምና ለውጭ አገራት በ15 ዶላር ለገበያ ቀርቧል፡፡ ደራሲው ከዚህ ቀደም “ከሜዳሊያው በስተጀርባ” የተሰኘ መፅሀፍ ለንባብ ማብቃቱ ይታወሳል፡፡

 በአካል ጉዳተኞች ላይ የሚሰሩ የ26 ድርጅቶች ጥምረት የሆነው “የኢትዮጵያ ናሽናል ዲሴቢሊቲ አክሽን ኔትወርክ (ኢንዳን)” የዓለም የሴቶች ቀንን (ማርች 8) ምክንያት በማድረግ የፊታችን አርብ በኢትዮጵያ ብሄራዊ ባህል ማዕከል የአካል ጉዳተኛ ሴቶች የዳንስ ትርኢት ያቀርባል፡፡  ለግማሽ ቀን በሚቆየው በዚህ የሴቶች ቀን አከባበር ላይ አካል ጉዳተኛ ሴቶች ያለባቸውን ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ ችግሮችና መፍትሄዎቻቸውን የሚመለከቱ ጥናታዊ ፅሁፎች የሚቀርቡ ሲሆን በፅሁፎቹ ላይ ውይይትና ሌሎች ኪነ ጥበባዊ ዝግጅቶችም ይቀርባሉ ተብሏል፡፡

 እናት የማስታወቂያ ድርጅት ከጀመርን የባህል ማዕከል (ጎተ) ጋር በመተባበር ነገ ከቀኑ 8፡00 በወመዘክር አዳራሽ ‹‹መስቀል አደባባይ›› በተሰኘው የግጥም መድበል ላይ ውይይት ያካሄዳል፡፡ መድበሉ የተለያዩ ወጣት ገጣሚያን የግጥም ሥራዎች ስብስብ ነው ተብሏል፡፡ ለውይይቱ የመነሻ ሀሳብ የሚያቀርቡት ዶ/ር በድሉ ዋቅጅራ መሆናቸውን የጠቆመው የውይይት አዘጋጁ፤ ፍላጎት ያለው በውይይቱ ላይ እንዲሳተፍ ጋብዟል፡፡

 “ስደት የሚለው ቃል በእርስዎ ምን ትርጉም አለው? አንድ ቀን እሰደዳለሁ ብለው ያስባሉ?” በሚሉና ሌሎች
ስለስደት የተነሱ ጥያቄዎች ላይ በዓለም ያሉ ከ40 በላይ ደራሲያንና ምሁራን የሰጧቸው መልሶች የተካተቱበት
የፖስተር ኤግዚቢሽን፣ ነገ በጀርመን የባህል ማዕከል (ጎተ) ከረፋዱ 4 ሰዓት ጀምሮ ይከፈታል፡፡
   በመክፈቻው ሥነ-ስርዓት ላይ ደራሲያን፣ ምሁራን፣ በስደት ላይ የሚሰሩ ድርጅቶች እንዲሁም ጥሪ የተደረገላቸው እንግዶች የሚታደሙ ሲሆን ታዋቂው ደራሲ፣ ሀያሲና ጋዜጠኛ ዓለማየሁ ገላጋይና ደራሲ ሰዓዳ መሀመድ፤ “ስደት በኢትዮጵያ የስነ-ፅሁፍ ስራዎች ውስጥ እንዴት ይታያል” በሚል ርዕስ ጥናታዊ ፅሁፎች እንደሚያቀርቡና ውይይት እንደሚደረግባቸው የጀርመን የባህል ማዕከል፣ የመረጃና የቤተ መፅሀፍት አገልግሎት ኃላፊ፣ አቶ ዮናስ ታረቀኝ ለአዲስ አድማስ ገልፀዋል፡፡

 --- መሣሪያዎቻቸውንና ልብሶቻቸውን በሲቪሎች የተነጠቁ ብዙዎች ተራፊዎች የለበሱት ቡቱቶ ነበር፣ ጥቂቶቹም እርቃናቸውን ነበሩ። አንዳንዶቹ ደግሞ ተሰልበዋል፤ከመሀላቸው አንዱ እሱን በኃይል ለመቆጣጠር ስምንት ሰዎች እንዳስፈለጉ ሲፎክር ነበር፡፡ ‹‹እጆቼ ደህና ናቸው›› ሲል ጮኸ፡፡ ‹‹ስድን ሁሉንም አቢሲኒያውያን መፍጀት እፈልጋለሁ…››
በዮሐንስ ዘመን የንጉሣዊ ግዛቱ ዋና ከተማ የነበረችው መቀሌ የተወሰነ ትኩረት ያላት ከተማ ነበረች፡፡ በ1895 የታህሳሥ ወር አብዛኛውን ጣልያኖቹ መከላከያዎችን ገነቡ። አንድ ቤተክርስቲያን የጥይት ማከማቻ ሆነ፡፡ የጣልያን ወታደሮችና አስካሪ ምልምሎቻቸው ዋና መከላከያቸው የሚሆነውን 230 ጫማ ርዝመት ያለውን ግምብ ሲገነቡ፣ ጣልያንኛ ዘፈኖችን ይዘፍኑ ነበር፡፡ ግንቦቹ ሲጠናቀቁም ግዙፍ ሆኑ፡፡ የኢትዮጵያን ቀላል መሣሪያዎች ከላይ በኩል ስድስት ጫማ፣ ከስር ደግሞ አስራ ስድስት ጫማ ውፍረት ያለውን ግምብ ለመደርመስ አስቸጋሪ ይሆንባቸዋል፡፡
የተከላካዮች ተስፋ የኢትዮጵያ ጦር አዛዦች በሰው ብዛት ምሽጉን ለመስበር እግረኛ ወታደሮችን በማከታተል ይልካሉ የሚል ነበር፡፡ የኢትዮጵያ የእግረኛ ጦር ጥቃት የጣልያን መድፎች ሥራቸውን እንዲሠሩ ያደርጓቸዋል፡፡ ጣልያኖቹ ለዚህ ዓይነት ፍልሚያ የተዘጋጁት በጥንቃቄ ነበር፡፡ ለአጥቂዎቹ ሽፋን ሊሆኑ የሚችሉና ለጣልያን መድፍ የእይታ መስመር የሚከልሉ ምሽጉ አካባቢ የነበሩ ጎጆዎችን አፈረሱ፡፡ ከምሽጉ ውጪም የመከላከያ ክልል በሽቦ አጠሩ፡፡ ከደቡብ በኩል ወደ ምሽጉ ዋና መዳረሻ፣ ግራና ቀኝ ኢንጂነሮች ጥልቅ ምሽጎች ቆፈሩ፡፡ እነዚህ አሥር ጫማ ጥልቀት ያላቸው ምሽጎች ስር በየሁለት ጫማ ርቀት አንድ፣ አንድ ሜትር የሚረዝሙ ሹል እንጨቶች ቀበሩ፡፡ ከደቡብ አቅጣጫ ወደ ምሽጉ የሚንደረደሩ የኢትዮጵያ ወታደሮች ሹል እንጨት የተሰካባቸው ምሽጎች አልፎ ለመሄድ ወደ መንገዱ መውጣት ይኖርባቸዋል፡፡ እንዲህ ሲያደርጉም ለጣልያን ተኩስ ምቹና ሰብሰብ ያሉ ኢላማዎች ይሆናሉ፡፡
ተርፈው ወደ ምሽጉ ግምቦች የሚጠጉ ወታደሮች፣ተጨማሪ አደጋዎች ይገጥሟቸዋል፡፡ የኢትዮጵያ ወታደሮች የሚዋጉት ባዶ እግራቸውን ነበር፡፡ ስለሆነም ጣልያኖቹ የጠርሙስና የሸክላ ስብርባሪዎችን በመንገዱ ላይ በተኑ። ኢትዮጵያውያኑ አደጋዎቹን አልፈው ከሄዱም ለጣልያን አልሞ ተኳሾች ይጋለጣሉ፡፡
አንድ ምሽግ ራሱን የቻለ ተቋም ነው፡፡ ሆኖም አብዛኛውን ጊዜ እንዲህ አይሆንም፡፡ ታህሣሥ ዘጠኝ አንድ ቡድን ለሰዎቹ ምግብ፣ ለእንስሶቹ መኖ ፍለጋ ምሽጉን ለቆ ወጣ፡፡ የቡድኑ አባላት በፍለጋቸው የተገነዘቡት ነገር አብዛኛው የአካባቢው ህብረተሰብ መሰወሩን ነው፡፡ ይህ የወታደሮቹን ሥራ ይበልጥ አስቸጋሪ አደረገው፡፡ የአካባቢ ገበሬዎችን እቃዎቻቸውን እንዲለዋወጡ፣ እንዲሸጡ ከማሳመን ይልቅ ወታደሮቹ ገበሬዎቹ ምግባቸውንና የከብት መኖውን የት እንደ ደበቁ ለማሰስ ተገደዱ፡፡
እነኚህ የምግብ ፍለጋ ተልዕኮዎች ቀጠሉ፡፡ የእንቅስቃሴው ክልል መስፋት ነበረበት፡፡ ውሎ አድሮ እነኚህ የምግብ ፍለጋ እንቅስቃሴዎች ከምሽጉ በስድስት ማይል ርቀት ተለጠጡ፡፡ ሌሎች የመጥፎ ገድ ምልክቶችም ነበሩ፡፡ ከሰሜኑ ጋር ያለው ግንኙነት የማያስተማምን ሆኗል፡፡ ከአምባ አላጌ በኋላ የአካባቢው ህብረተሰብ አምርሯል፡፡ በቀን የሚጓጓዙ መልእክተኞች እንቅፋቶች ገጠሟቸው፡፡ ማለፍ የሚችለው በሌሊት የሚጓጓዝ ደብዳቤ ብቻ ሆነ፡፡
በየቀኑ በሚሰጣቸው የወይን ጠጅ፤ የቡናና የመጠጥ ራሽን ሳቢያ የጣልያኖች መንፈስ የተነቃቃ ነበር፡፡ ለአውሮፓውያን ወታደሮች በተጨማሪ ሲጋሮችና ትምባሆ ይሰጧዋል፡፡ ወታደሮቹ በጭንቀትና በመጠጥ በመገፋፋት ኢትዮጵያውያኑን እንዴት እንደሚፈጇቸው ጉራ ይቸረችራሉ። ‹‹አቢሲኒያዎች! የገሃነምን መንገድ እንድታገኙ እንረዳችኋለን!›› ሲል አንዱ ጮኸ፡፡ ማታ ማታ አውሮፓውያን መኮንኖች ተሰብስበው እየጠጡ ይጮኹ ነበር፡፡
‹‹የቺያንቲ ፋሽኮዎች፣ የባርቤራ ጠርሙሶች በጠረጴዛ ስር ተንከባለሉ›› ሲል አንድ መኮንን ያስታውሳል፡፡ ‹‹ረጅም ዕድሜ ለጣልያን! ረጅም ዕድሜ ለንጉሥ ኡምቤርቶ! ረጅም ዕድሜ ለሜጀር ጋሊያኖ! ረጅም ዕድሜ ለሜጀር ቶዜሊ!›› እያሉ ይጮሁ ነበር፡፡ ሜጀር ቶዜሊ ለጄኔራል ባራቲዮሪ በቃላት የተዋበ ዘገባ ላከ፡፡ ‹‹ሞራል እስከ ጫፍ ተሰቅሏል፡፡››
ታህሳስ 19 ይህ ሁሉ መንፈስ በአስደናቂ ሁኔታ ተለወጠ፡፡ ጠዋት አራት ሰዓት አካባቢ በደቡብ ምሥራቅ በሸለቆው ዳርቻ፣ ከፍታው ወደሜዳው በሚያዘቀዝቅበት አካባቢ ከፍተኛ የአቧራ ደመና ተነሳ፡፡ መሠረቱ በእግርና በፈረስ የሚተም ግዙፍ የጦር ክፍል ቅርፅም ያዘ፡፡ የራስ መኮንን ጦር ከአምባ አላጌ ድሉ እየተመለሰ ነበር፡፡
(በሬይሞንድ ጆናስ ከተጻፈውና በኤፍሬም እንዳለ ከተተረጎመው “የአድዋ ጦርነት”
መጽሐፍ የተቀነጨበ፤ 2009)

Thursday, 09 March 2017 07:50

“ሆድ ይፍጀው... ብዬ”

   እኔ በልጅነቴ ነበር አክስቴ ወደምትኖርበት ውጭ ሀገር ሄጄ የሰው ቤት ስራ እንድሰራ ሁኔታዎች የተመቻቹልኝ። የዚህም ምክንያት በትዳር አለም ስኖር ሁለት ልጆችን ከወለድሁ በሁዋላ ባለቤ በመሞቱ ነበር። በሁዋላም ወደውጭ ሀገር ሄጄ ስራዬን በመስራት ላይ እንዳለሁ የአሰሪዬ ዘመድ የሆነ ሀብታም ለትዳር እፈልጋታለሁ በማለቱ ተዳርኩለት። በዚህ ሁኔታ እንዳለን ታሪኬን አጫወትኩት። ልጆቼን ወስጄም እንዳስተምራቸው ፈቀደልኝ። በደስታ ወደምኖርበት ሀገር ወስጄ ሁለቱንም ትምህርት ቤት አስገባሁዋቸው። ሲውል ሲያድርም ልጆቹ አደጉ። አማረባቸው። በተለይም ሴትዋ በጣም ውብ ሆነች። ሰው ማንን ይመስላል ሲባል ኑሮውን ...ተብሎ የለ? ነገር ግን ሁኔታዎች መልካቸውን እየቀየሩ መምጣታቸው አልቀረም። ባለቤ ልጄን አስገድዶ ደፈራት። እኔም ኡኡ የአገር ያለህ አልል...ያለሁት እሰው ሀገር...ማን ሰሚ ይኖረኛል? እንዲሁ እዬዬ እያልኩ ያገናኙንን ሰዎች ሽምግልና ብልክበት...እኔ ልጅ እፈልጋለሁ። እስዋ ደግሞ አልወልድልህም ብላኛለች...ስለዚህ ...በቃ ...እክሳለሁ...አለ። እኔም ለጊዜው ልጄን ይዤ ወደሐገር ቤት መጣሁ። እውነትም ጸንሳ ኖሮአልና ምንም ማድረግ አልቻልኩም። በ17/አመት እድሜዋ የተደፈረችውን ልጄን የጸነሰችውን ልጅም በሰላም ተገላግላ እንድታሳድግ በሚል ተለመንኩና... የተሰጠኝን ካሳ ተቀብዬ ...ሆድ ይፍጀው...ብዬ እንደገና ልጄን ለባሌ በሕግ አፈራርሜ ዳርኩለት። እሱዋም በመጀመሪያው ወንድ ልጅ ከዚያም ሴት ልጅዋን ወልዳ ትዳር ከተባለ ትዳርዋን ይዛ ቁጭ ብላለች። አኔም ከሀያ አመት በላይ ከኖርኩባት ሀገር ለአንዴና ለመጨረሻ ጊዜ ትቼ ወደሀገር ቤት ተመልሻለሁ። አያሳዝንም?
 ወ/ሮ ፈትለወርቅ ከአዲስ አበባ።
አለምአቀፉ (Behavioral social and movement sciences ) በ2014 አንድ ጥናት አውጥቶአል። ይህ ጥናት እንደሚገልጸውም አስገድዶ መድፈር በአሁኑ ወቅት አለም አቀፍ ችግር እንደሆነ ነው። እንዲያውም ጥናቱ እንደሚገልጸው ካለጥርጥር በአለማችን እየተካሄዱ ካሉ ጦርነቶች እንደአ ንዱ ሊቆጠር ይችላል። ምንም እንኩዋን በሴቶች መብት ላይ አመታትን ያስቆጠረ የግንዛቤ መፍጠሪያ መድረኮችና ንቃተ ሕሊናን የሚያዳብሩ ስራዎች ቢሰሩም ዛሬም ሴቶችንና ልጃገረዶችን የመድፈር ሁኔታ በመቀጠሉ እንደ አንዱ የስነዋልዶ ጤና ችግር መንስኤ ሆኖ ከማስቸገሩም በላይ ምናልባትም ከህብረተሰቡ ማግኘት የሚገባውን የመከላከል ስራም አላገኘም ማለት ይቻላል ይላል ጥናቱ። በእርግጥ አስገድዶ መድፈር ከቦታ ቦታ እና እንደየህብረተሰቡ የኑሮ ልምድ እና እንደየሀገራቱ የህግ አተረጉዋጎም የተለያየ ትርጉም የሚሰጠው ነው። በአጠቃላይ ግን አስገድዶ መድፈር ወንድ በሴት ላይ የሚያደርሰው ጉዳት የከፋ ሆኖ ቢታይም ሴቶችም አልፎ አልፎ በወንዶች ላይ የሚፈጽሙት ሆኖ ይስተዋላል። ወደጥናቱ ዝርዝር ስንገባ በመጀመሪያ የአስገድዶ መድፈር ሁኔታ እና የደፋሪዎች ማንነት ይቀድማል።
የአስገድዶ መድፈር እና የደፋሪዎች አይነት
Zanni(2009) ዛኒ የተባለች ተመራማሪ ለአለም የጤና ድርጅት ባቀረበችው ምርምር እንደገለጸ ችው ጥቃት አድራሾች በተለያዩ ቡድኖች ይከፈላሉ ትላለች።
Stranger Rape - በማይተዋወቁ ሰዎች መካከል የሚደርስ የጾታዊ ጥቃት አይነት ነው። ይህም ማለት ጥቃት አድራሹም ሆነ ጥቃት የሚፈጸምበት ሰው ቀደም ሲል ምንም አይነት ትውውቅ የሌላቸውና በአጋጣሚ የሚፈጸም ነገር መሆኑን ነው።
Acquaintance rape - ጥቃት አድራሹ እና ጥቃት የሚፈጸምበት ሰው አስቀድሞውኑ ትውውቅ ያላቸውና ያንን መሰረት በማድረግም የሚፈጸም ነው። ይህ ትውውቅም ምናልባትም በቀድሞው ጊዜ እጮኛነት ወይንም የፍቅር ግንኙነት የነበራቸው እንዲሁም የግብረስጋ ግንኙነት አድርገው የሚያውቁ ሰዎች ሊሆኑ ይችላሉ።
Partner rape - አብረው በሚኖሩ ሰዎች መካከል የሚፈጸም ነው። ሁለቱ ሰዎች አብረውየኖሩት በባልና ሚስትነት ሊሆን ይችላል። ወይንም በዩኒቨርስቲዎች ውስጥ ወይንም በስራ አጋጣሚ በአንድ ጣሪያ ስር የሚኖሩ ሊሆኑ ይችላሉ። በኑሮ አጋጣሚም በቤት ውስጥ በዘመዳሞች መካከል የሚፈጠር አስገድዶ መድፈር ሊሆን ይችላል።
Gang Rape - ሌላው አስገድዶ መድፈር የመፈጸም ሁኔታ የተወሰኑ ወንዶች በቡድን ሆነው የሚፈጽሙት ነው። ይሄም ሰዎቹ ለምንድነው እንዲህ ያለ ጥቃት የሚፈጽሙት ተብሎ ሲጠየቅ በልጅነት ዘመናቸው ወይንም ደጉም በሁዋላ በህብረት ወንጀል መፈጸ ምን እያዳበሩ የመጡ መሆናቸውን ነው መረጃዎች የሚጠቁሙት። በአባቢ፣ በዘር ወይንም በትምህርት ቤት በመሳሰሉት እነእገሌ እኮ ኃይለኞች ወይንም ጎበዞች ናቸው ተዋጊዎች ናቸው የሚል አይነት መገለጫን እያዳበሩ የመጡ ሰዎች ናቸው አስገድዶ መድፈር ወንጀልን የሚፈጽሙት። እንደዚህ ያለው ወንጀል በተለያዩ የአፍሪ አገሮችና በሌሎችም የሚታይ ነው። አንዱ ሌላውን ከመዋጋት ይልቅ የተቃራኒውን ወገን አስገድዶ በመድፈር ሃይልን መወጣት ይበልጥ የሚያስደስትበት ሁኔታ ይታያል።
የተለያዩ መረጃዎች እንደሚገልጹት አልኮሆል ወይንም ሱስ አስያዥ እጽን መጠቀም አንዱ ለአስገድዶ መድፈር የሚዳርግ ነገር ነው። ሰዎች በተፈጥሮ ህብረተሰቡ የሰጠውን ሁኔታ ተቀብሎ በማደግ ያልሆነ ነገር ውስጥ እንዳይገቡ የሚመልሳቸው በጭንቅላት ውስጥ የሚገኝ ተፈጥሮአዊ ነገር አለ። ያ ተፈጥሮአዊ ነገር ድርጊትን ለመፈጸም በሚፈለግበት ጊዜ ይሄ ትክ ክል አይደለም ይሄ ትክክል ነው የሚል ከመጥፎ ነገር የሚከላከለ ነው። አልኮሆል ወይንም ሱስ አስያዥ ንጥረ ነገር ግን ይህንን ጥሩና መጥፎ ነገር አመላካች የሆነውን ነገር በማደብዘዝ ይገታዋል። ስለሆነም ይህንን ነገር ማድረግ የለብኝም ያስቀጣኛል ወይንም ሰው እጎዳለሁ ወይ ንም ህብረተሰቡ ይህንን ድርጊት ያወግዘዋል ብሎ ለመተው ከመሞከር ይልቅ እንዲያውም ድርጊቱን ለመፈጸም የሚገፋፋ የሚያደፋፍር ነገር ይፈጠራል።
ወንድ ሴትን የሚደፍረው ብዙ ጊዜ የስርአተ ጾታ ክፍፍል ልዩነቱ ወይንም ጀንደር ከሚለው ሁኔታ ጋር ይያያዛል። ሴት እንዲህ ነች ወንድ ደግሞ እንዲህ ነው የሚለውን ህብረተሰቡ የሚያምንበትና ተግባራዊ እያደረገው ለው ጋር በተያያዘ አስገድዶ መድፈሩ ብዙ ጊዜ ይፈጸማል። ምክንያቱም ህብረተሰቡ ለወንድ ልጅ ኃይል ወይንም አቅም እንዳለው እየነገረ ስለሚያሳድገው ወንዱ በተፈጥሮው ገኘው ጥንሬ ባሻገር በአስተሳሰብም ኃይል እንዲኖረው ያደርገዋል።ከዚህም በተለየም በልጅነታቸው የመደፈር ወይንም የመገለል እንዲሁም የተለያዩ ጥቃቶች የደረሰባቸው ከሆነ አስገድዶ መድፈርን እንደ እልህ መወጫ ይጠቀሙበታል። አንድ ወንድ እንደዚህ ያለ ጉዳት እየደረሰበት ያደገ ከሆነና እሱም ጥቃቱን መፈጸሙ በሳይንሳዊው መንገድ ሲተረጎም አእምሮው በሚያድግበት ሰአት የተለያዩ ኢንዛይሞች ማለትም ነርቭ ከነርቭ የሚገናኝበት መልእክት የማስተላለፊያ ኬሚሎች በደም ውስጥ እየቀነሰ ይመጣል። አእምሮው እያደገ ሲመጣ ደሙ ግን እየቀነሰ መምጣቱ በሚያድጉበት ሰአት ላይ ይህንን ወሲባዊ ጥቃትም ሆነ ማንኛውንም ወንጀል እንደሰው መግደል የመሳሰሉትን ጨምሮ የመፈጸም እድላቸው የሰፋ ይሆናል። ብዙ ጊዜ አስገድዶ መድፈር የሚፈጽሙ ሰዎች ከአንድ ሰው ጋር ወይንም ከተለያዩ ሰዎች ጋር ጥሩ አይነት ግንኙነት መመስረት የማይችሉ ናቸው። ይህ እንግዲህ ከአስተዳደግ ወይንም ከተለያዩ የህይወት አጋጣሚዎች ሊሆን ይችላል። በተረጋጋ ሁኔታ ከሰዎች ጋር መኖር ልተቻለ ወይንም ህብረተሰቡ የሚጠብቀውን ደረጃ ማሟላት ልተቻለ እንደመሸሻ የሚቆጠረው የአስገድዶ መድፈር ወንጀልን የመሳሰሉ ሊሆኑ ይችላሉ።
 ዶ/ር ዳዊት ደሳለኝ
 የጽንስና ማህጸን ሕክምና እስፔሻሊስት
Alexis (2009) እንደምትገልጸው የወሲብ ጥቃት አድራሾች ወይንም አስገድደው ደፋሪዎች በሶስት ይከፈላሉ።
Power rapist :- ጉልበት የማሳየት ወይንም እኔ ከእገሌ እበልጣለሁ ስለዚህም ማሳየት አለብኝ ከሚል የተሳሳተ አስተሳሰብ የሚመነጭ ሲሆን የሚረኩትም ጾታዊ ግንኙነት በማድረጋቸው ሳይሆን የበላይነትን በማሳየታቸው ነው።
Opportunist rapists:- የሚባሉት ደግሞ የሚፈልጉዋትን ሴት ለረጅም ጊዜ ሲከታተሉ ቆይተው ሁኔታዎች ሲፈቅዱ የወሲብ ጥቃት የሚያደርሱ ናቸው።
Entitlement rapists :- የሚባሉት ደግሞ ሴትዋ ፈለገችም አልፈለገችም ወሲባዊ ግንኙነት ማድረግ የወንድ ልጅ መብቱ ነው ብለው የሚያስቡ ናቸው።
“አስገድዶ መድፈርን የሚፈጽሙት ወንዶች የግብረስጋ ግንኙነትን ፈልገው ሳይሆን ኃይልን ለመግለጽ የሚያደርጉ ሲሆን በዚሁ አጋጣሚ ግን አንዳንድ ጊዜ ሴቶች ተገደው እየተደፈሩ ሳሉ ወደ ወሲባዊ ስሜት የሚገቡበት ሁኔታ መኖሩም ተረጋግጦአል።
ሴቶቹ በዚህ ስሜት ምክንያት ማለትም ተገድጄ እየተደፈርኩ ግን ደስተኛ ሆንኩ በሚል ብዙ ጊዜ እራሳቸውን ያማርራሉ። ነገር ግን እንዲህ ያለው ነገር የሚከሰተው ስሜቱ ከተፈጥሮ ቁጥጥር ውጭ በመሆኑ ነው። ይሄ ሁሉም ተገደው የሚደፈሩ ሴቶች ላይ የሚኖር ሳይሆን አንዳንድ ሴቶች ላይ የሚፈጠር ነው። ወንዶቹም አስገድደው በሚደፍሩበት ጊዜ ኃይላቸውን አሳይተው ይተዋሉ እንጂ የዘር ፈሳሽ እስኪለቁ ድረስ ወሲባዊ ግንኙነቱን እያደረጉ አይቆዩም።”
ዶ/ር ዳዊት ደሳለኝ
የጽንስና ማህጸን ሕክምና እስፔሻሊስት