Administrator

Administrator

የሩሲያው ፑቲንና የግብጹ አልሲሲም ለሽልማት ታጭተው ነበር

   አለማቀፉ የፕሬስ ነጻነት መብቶች ተሟጋች ተቋም ሲፒጄ ለመጀመሪያ ጊዜ ይፋ ባደረገው “የአለማችን ቀንደኛ የፕሬስ ነጻነት ጨቋኝ መሪዎች”  ልዩ ምጸት አዘል ሽልማት፣ የአሜሪካው ፕሬዚዳንት ዶናልድ ትራምፕና የቱርኩ አቻቸው ጠይብ ኤርዶጋን በተለያዩ ዘርፎች አሸናፊዎች መሆናቸው ተነግሯል፡፡
ዶናልድ ትራምፕ “የአመቱ ምርጥ ውሸታም ሚዲያዎች ሽልማት” የተሰኘና በአይነቱ ልዩ የሆነ ሽልማት በማዘጋጀት በመጪው ሳምንት አሸናፊዎችን ይፋ እንደሚያደርጉ ባለፈው ሰኞ ማስታወቃቸውን ተከትሎ፣ ተቀማጭነቱን በኒውዮርክ ያደረገው ሲፒጄ፤ ዶናልድ ትራምፕ ከጋዜጠኞች የሚሰነዘሩባቸውን ትችቶች እየተከታተሉ በማፈንና የዜጎችን ሃሳብን በነጻነት የመግለጽ መብቶች በመጣስ፣ ከአለማችን መሪዎች ሁሉ አቻ ስለሌላቸው ሸልሜያቸዋለሁ ብሏል፡፡
ፕሬዚዳንት ትራምፕ በተጠናቀቀው የፈረንጆች አመት 2017፣ በተለያዩ የህትመትና የኤሌክትሮኒክስ መገናኛ ብዙሃን ላይ እከስሳችኋለሁ ወይም የሥራ ፈቃዳችሁን እነጥቃችኋለሁ በሚል በተደጋጋሚ ዝተዋል ያለው ተቋሙ፤ ትራምፕ ባለፉት ሁለት አመታት ጊዜ ውስጥ በትዊተር ባስተላለፏቸው ከ1 ሺህ በላይ መልዕክቶች፣ መገናኛ ብዙሃንን መዝለፋቸውንና ማስፈራራታቸውን አስታውሷል፡፡ ጋዜጠኞችን ከስራ ትባረራላችሁ ሲሉ በይፋ አስፈራርተዋል፤ ተመልካቾች አንዳንድ የመገናኛ ብዙሃንን እንዳይከታተሉ ጥሪ አቅርበዋል፤ ለዚህ ሁሉ ድርጊታቸው ሸልሜያቸዋለሁ ብሏል ሲፒጄ፡፡
የጸረ-ሽብር ህጎችን በመጠቀም የፕሬስ ነጻነትን በማፈን ዘርፍ፣ የቱርኩ ፕሬዚዳንት ጠይብ ኤርዶጋን የተሸለሙ ሲሆን በዚሁ ዘርፍ ታጭተው የነበሩት የግብጹ አብዱል ፈታህ አልሲሲ ለጥቂት ተሸንፈዋል ያለው ሲፒጄ፤ በግብጽ ባለፈው የፈረንጆች አመት 2017 ብቻ ከ20 በላይ ጋዜጠኞች መታሰራቸውን አመልክቷል፡፡
በሚዲያ ላይ ጥብቅ ቁጥጥር በማድረግ የቻይናው ፕሬዚዳንት ዢ ጂፒንግ ሲሸለሙ፣ የሩሲያው ፑቲን ድል ሳይቀናቸው ቀርቷል፡፡ ቭላድሚር ፑቲን ወደ ስልጣን ከመጡ በኋላ የሚገደሉ፣ የሚታሰሩና ጥቃት የሚደርስባቸው የሩሲያ ጋዜጠኞች ቁጥር እየጨመረ ነው፤ የአገሪቱ ነጻ ሚዲያም እየቀጨጨ መሄዱን ቀጥሏል ያለው ተቋሙ፤በአለማችን ላይ ለእስር የተዳረጉ ጋዜጠኞች ቁጥር በ2017 ከፍተኛው ደረጃ ላይ መድረሱን አስታውቋል፡፡ በአመቱ በአለማችን የተለያዩ አገራት 262 ጋዜጠኞች በእስር ላይ ነበሩ ብሏል - ሲፒጄ፡፡

 የቱኒዝያ መንግስት ግብር ለመጨመር ከያዘው አዲስ እቅድ ጋር በተያያዘ ባለፈው ሰኞ የተቀሰቀሰው ተቃውሞ በከፍተኛ ሁኔታ እየተስፋፋ መሄዱን ተከትሎ፣ ባለፈው ረቡዕ ምሽት ብቻ ከ330 በላይ ዜጎች ለእስር መዳረጋቸውንና ባለፉት ቀናት የታሰሩት ሰዎች ቁጥር ከ600 በላይ መድረሱን ሮይተርስ ዘግቧል፡፡
የአገሪቱ ጠቅላይ ሚኒስትር ዮሱፍ ቻሄድ፣ ተቃዋሚ ፓርቲዎች ዜጎችን ለከፋ ጥፋት እያነሳሱ መሆናቸውን በማውገዝ፣ ዜጎች ከህገወጥ ድርጊታቸው እንዲታቀቡ ጥሪ ያቀረቡ ሲሆን የአገር ውስጥ ጉዳይ ሚኒስትር ቃል አቀባይ ካሊፋ ቺባኒ በበኩላቸው፤ረቡዕ ምሽት በቁጥጥር ስር የዋሉት 330 ሰዎች ተቃውሞውን ያቀናበሩና ግርግሩን ሽፋን በማድረግ የዝርፊያ ድርጊት ሲፈጽሙ የተገኙ ናቸው ማለታቸውን ዘገባው ጠቁሟል፡፡
የአገሪቱ ዜጎች በዋጋ መናርና እየከፋ በመጣ የስራ አጥነት በተማረሩበት ወቅት መንግስት በዜጎች ላይ የግብር ጫና ለማድረግ ማሰቡ ብዙዎችን ማስቆጣቱንና በመዲናይቱ የተቀሰቀሰው ተቃውሞ ሳምንቱን ሙሉ በመቀጠል ወደ ሌሎች ከተሞች መስፋፋቱን፣ የአገሪቱ መንግስትም እጅግ በርካታ ቁጥር ያላቸውን ወታደሮች አሰማርቶ፣ ተቃውሞውን ለማብረድ እየተንቀሳቀሰ እንደሚገኝ ዘገባው አመልክቷል፡፡
ተቃዋሚዎች በተለያዩ የአገሪቱ ከተሞች የደህንነት ቢሮ ህንጻዎችን ጨምሮ በርካታ የመንግስት ተቋማትን ማቃጠላቸውንና ወደተለያዩ ከተሞች የተስፋፋውና ታዋቂ የቱሪስት መዳረሻዎችን ጭምር ያጥለቀለቀው ተቃውሞ ተባብሶ በመቀጠሉ መንግስት በመቶዎች የሚቆጠሩ ወታደሮችን በመላ አገሪቱ ማሰማራቱንም ገልጧል፡፡
በቱኒዝያ በ2011 እና በ2015 የተካሄዱ ተቃውሞዎችና ጥቃቶች የአገሪቱን ኢኮኖሚ ስምንት በመቶ ድርሻ የሚሸፍኑትን የውጭ ኢንቨስትመንትና የቱሪዝም ዘርፎችን በከፍተኛ ሁኔታ ማውደማቸውንም ዘገባው አስታውሷል፡፡
በተያያዘ ዜና፣ በኢራን ባለፉት ሁለት ሳምንታት በተካሄዱ ጸረ-መንግስት የተቃውሞ ሰልፎች ላይ ተሳትፋችኋል በሚል በፖሊስ ቁጥጥር ስር የዋሉት ዜጎች ቁጥር 3 ሺህ 700 እንደሚደርስ፣ አንድ የአገሪቱ ከፍተኛ የህግ ባለሙያ ማስታወቃቸውን ቪኦኤ ዘግቧል፡፡
በኢራን በተቃውሞ ተሳትፋችኋል በሚል ከተያዙት ዜጎች መካከል አምስቱ በእስር ላይ ሳሉ ለህልፈተ ህይወት ተዳርገዋል ያለው አለማቀፉ የሰብዓዊ መብቶች ተሟጋች አምነስቲ ኢንተርናሽናል፤ የኢራን መንግስት ያሰራቸውን ዜጎች በአፋጣኝ እንዲፈታ ጥያቄ ማቅረቡን ዘገባው አመልክቷል፡፡
በእስር ላይ በሚገኙ ዜጎች ላይ አሰቃቂ ድብደባ እየደረሰ ነው፣ እስር ቤቶቹ የሚገኙበት ሁኔታም እጅግ አስቸጋሪና ስቃይ የሞላበት ነው የሚለው  አምነስቲ፤ ጉዳዩ በአፋጣኝ በገለልተኛ ወገን  እንዲጣራና በእስረኞች ላይ ግፍ የሚፈጽሙ አካላትም ለህግ እንዲቀርቡ ጠይቋል፡፡

 ደራሲ ከበደ ሚካኤል ከፃፏቸው አጫጭር ትርክቶች መካከል የሚከተለው ይገኝበታል፡፡
ከዕለታት አንድ ቀን አንድ ፈረሰኛ ተራራ እየወጣ ሳለ፤ አንድ፣ አንድ እግሩ ቆራጣ የሆነ ሰው ያንን መንዲስ የሚያክልና ጫፉ ሩቅ የሆነ ተራራ፤ እየተንፏቀቀ ለመውጣት ሲፍጨረጨር ያገኘዋል፡፡ ያም እግሩ የተቆረጠ ሰው፡-
“ጌታዬ እባክህ የተወሰነ መንገድ ድረስ አፈናጠኝና ውሰደኝ?” ሲል ይለምነዋል፡፡
ፈረሰኛውም ልቡ በጣም ይራራና፤ “እሺ ወዳጄ፤ ፈረሱ የቻለው ርቀት ያህል አብረንእንሄዳለን፡፡ ና ውጣ” ብሎ፤ ወርዶ፣ አቅፎ ያፈናጥጠዋል፡፡
ትንሽ መንገድ አብረው ከተጓዙ በኋላ፤ እግረ ቆራጣው ሰውዬ፤
“ጌታዬ፤ ብዙ ምቾት አልተሰማኝም፡፡ አካል-ጉዳተኛ በመሆኔ አንደኛው እግሬን እጅግ ህመም ተሰማኝ!” አለው፡፡
ፈረሰኛው፤
“ታዲያ እንዴት ብናደርግ ይመችሃል?” ሲል ጠየቀው፡፡
አካል-ጉዳተኛውም፤
“ትንሽ መንገድ እኔ ልሂድ፣ አንተ እግርህ ጤነኛ ስለሆነ ተከተለኝ” አለው፡፡
ፈረሰኛው በሁኔታው አዝኖ ልቡ ራራና፤
“መልካም፤ እኔ ልውረድ አንተ ሂድ፡፡ ሲደክመኝ ትጠብቀኝና ደሞ አብረን እንጓዛለን” አለውና ወረደ፡፡
የተወሰነ ርቀት፤ አካል-ጉዳተኛው በፈረስ፣ ባለፈረሱ በእግሩ ተጓዙ፡፡
ፈረሰኛው “ደክሞኛል ጠብቀኝ” አለው፡፡
እንደገና ተፈናጠጡና መንገድ ቀጠሉ፡፡ ጥቂት እንደተጓዙ፣ ፈረሰኛው ወረደለትና አካል ጉዳተኛው በፈረስ ቀጠለ፡፡ አሁን ግን ያ አካል-ጉዳተኛ ፈረሱን ኮልኩሎ ለዐይን ተሰወረ፡፡ ፈረሰኛው ቢሮጥ፣ ቢሮጥ ሊደርስበት አልቻለም፡፡
ባለፈረሱ  ጮክ  ብሎ፣ “እባክህ ሌላ ምንም አልፈልግም፣ የምነግርህን ብቻ አንዴ አዳምጠኝ?” አለው፡፡
ፈረስ ነጣቂው ባለቤቱ የማይደርስበት አስተማማኝ ቦታ ሲደርስ፤
“እሺ ምን ልትል ነው የፈለከው? እሰማሃለሁ ተናገር!” አለው በዕብሪት፡፡
ባለፈረሱም፤
“ወንድሜ ሆይ! አደራህን ይሄን እኔን ያደረከኝን ነገር ለማንም ሰው እንዳትነግር፡፡ ወደፊት በዓለም ደግ የሚያደርግ ሰው ይጠፋል!” አለው፡፡
*   *   *
ደግነት የብዙ ህይወታችን መሰረት መሆኑን አንዘንጋ፡፡ ቀናነት ካልተጨመረበት ዲሞክራሲም፣ ፍትሃዊነትም፣ ልማትም፣ አስተማማኝነቱ አጠያያቂ ነው፡፡ ደግ ያደረጉን ለመካስ ዝግጁ መሆን እንጂ ለክፉ ማጋለጥ አይገባም፡፡ ሁሉም የህብረተሰብ ክፍል በሀገሩ ጉዳይ ያገባዋል፡፡ መምህራን የልጆችን ተስፋ አለምላሚ ናቸው፡፡ ወታደሮች የሀገር ህልውና ጠባቂዎች ናቸው፡፡ ገበሬዎች የኢኮኖሚ ገንቢዎች ናቸው፡፡
የጥበብ ሰዎች የዘመን ዜማዎች ናቸው፡፡ ሁሉም የዴሞክራሲ ተቋዳሾች ናቸው፡፡  
“ሀብት ሲበዛ ዲሞክራሲ ይረጋገጣል ያለው ማነው?” ብሏል አንድ አዋቂ፤ ምን ያህል ፖለቲካና ኢኮኖሚ እንደሚተሳሰሩ ሲያጠይቅ! ያለው ይናገራል፣ የሌለው ያፈጣል ወይም ሁሉን “እሺ” ይላል፤ የሚባል ነገር አለና አስተውለን ብናስብ ታላቅ ነገር ነው፡፡ ዞሮ ዞሮ፤ እየተሳሰቡ መጓዝን የመሰለ ነገር የለም፡፡ መከራችን፤ የሀገራችን የችግር ቁልል ተራራ አካል ነውና ለብቻ አይገፋም፡፡
ከረዥም ጊዜው የኢትዮጵያ ወጣቶች ትግል አንፃር ስንመለከት ወጣቶች ልዩ ባህሪ እንዳላቸው እናስተውላለን - ታሪክን ዋቤ ቆጥረን፡፡ ባህሪያቸው፤ ቁርጠኝነትና ራስ - ወዳድ አለመሆን፣ ፍትሐዊነት፣ ጭቦኛ አለመሆን፣ የሴቶችን እኩልነት ማመን እና ትሁትነት የሚያካትቱ ልዩ ምልክቶቹ ነበሩ፤ ለማለት ያስደፍራል፡፡ እኒህ ምልክቶቹ ዛሬ ወዴት አሉ? ብሎ መጠየቅ ያባት ነው! እንጠያየቅ፡፡ ወጣቱን ያላቀፈ ጉዞ፣ ጉዞ አይደለምና!
አንጋረ ፈላስፋ፤
“ፀብ ክርክር ካለበት ጮማ-ፍሪዳ፤ ፍቅር ያለበት ጎመን ይሻላል” ይለናል፡፡ ፍቅርና መተሳሰብ የልማት፣ የኢኮኖሚ ድርና ማግ ናቸው እንደማለትም ነው፡፡ ባህልን ማክበር፣ አዋቂን ማድመጥ፣ ለዕውቀት መሪ ቦታ መስጠት፣ ጎረኝነትን ማስወገድና የጋራ መድረክ፣ የጋራ ሸንጎ መሻት፣ ዋና ጉዳይ መሆናቸውን መቼም አንዘንጋ፡፡
“የአያቴ ብስክሌት መንዳት አሪፍ መሆን እኔን ከመውደቅ አያድነኝም” ይላል ገጣሚ ሰለሞን ደሬሣ (ልጅነት)፡፡ በትላንት አበው ታሪክ መመካት ብቻውን ወደ ፊት አያራምደንም ሲል ነው፡፡ አንድም ነገን ዛሬ እንፍጠረው እንደ ማለት ነው፡፡ ለሁሉም እኩል የሆነች አገር አጠንክሮ ለመጨበጥ እንዘጋጅ ሲልም ነው፡፡ እርስ በርስ የማንፈራራባት፣ የማንጠራጠርባት፣ ነጋችንን ጨለማ አድርገን የማናይባት አገር ነው መገንባት ያለብን፡፡ ከሁሉም በላይ ግን፤ አለመተማመን ከመርገምት ሁሉ የከፋ መርገምት ነው፡፡ “ስንት ሰዓት ነው?” ቢሉ ከተሜው፤ “የዘመኑ ሰዓትና የዘመኑ ሰው ውሸታም ነው፡፡ ዝም ብለው ጥላዎትን አይተው ይሂዱ!” አለ ባላገር፤ የሚለው ቁም ነገር፣ ነገን እንድናስተውል ልብ በሉ የሚለን ነው!

 የአሜሪካ የውጭ ጉዳይ መሥሪያ ቤት፤ የዓለም ሃገራትን የፀጥታ ሁኔታ አስመልክቶ ባለፈው ረቡዕ ባወጣው የደረጃ ሰንጠረዥ፤ ኢትዮጵያን በጉዞ ወቅት የበለጠ ጥንቃቄ ማድረግ ከሚያስፈልግባቸው ሃገራት ተርታ መድቧታል፡፡
በደረጃ አንድ የተመደቡ ሀገራት የተለመደው ጥንቃቄ ተደርጎ ጉዞ ሊደረግባቸው የሚችሉ ሲሆን ኢትዮጵያ የተመደበችበት ደግሞ የፀጥታ ሁኔታቸው የሚያሰጋና በጣም ጥንቃቄ ሊደረግባቸው ከሚገቡ ሀገራት ተርታ ነው ብሏል- የአሜሪካ ድምፅ ባቀረበው ዘገባ፡፡
የግጭቶች የመከሰት እድሉ ከፍተኛ መሆኑንና  መንግስት ኢንተርኔት በተደጋጋሚ መዝጋቱ ሀገሪቱን በጣም ጥንቃቄ ማድረግ ከሚያስፈልጋቸው ሀገራት እንድትመደብ ዋና ምክንያት ሲሆን በአዲስ አበባ የሚገኘው ኤምባሲም በኢንተርኔት መቋረጥ ምክንያት ዜጎቹን በመረጃ መድረስ እንደማይችል ተጠቅሷል፡፡
አሜሪካውያን በኢትዮጵያ ቆይታቸው የሃገር ውስጥ መገናኛ ብዙኃን እንዲከታተሉና ለመረጃዎች ንቁ እንዲሆኑ የውጭ ጉዳይ መስሪያ ቤቱ አሳስቧል።
በኢትዮጵያ የሚገኙ የጉብኝትና የጉዞ አካባቢዎችንም በ4 ደረጃዎች መድቦ፣ ዜጎቹ ጉዟቸውን በጥንቃቄ እንዲያደርጉ ያሳሰበው መግለጫው፤ በአንደኛ ደረጃ የተመደቡት የተለመደ ጉዞ ማድረግ የሚቻልባቸው ሲሆን በኦሮሚያ ክልል ምስራቅ ሃረርጌና አፋር ክልል የደናክል አካባቢ በ3ኛ ደረጃ የተመደቡ መሆኑ ታውቋል፡፡ በ3ኛ ደረጃ የተመደቡ አካባቢዎች የሚደረጉ ጉዞዎችን ደጋግሞ በማሰብ፣ እስከመሰረዝ የሚገቡ ናቸው ይላል ሪፖርቱ፡፡
ከፍተኛ የሆነ የደህንነት ስጋት ያለባቸው የምስራቅ ሃረርጌ አካባቢ ግጭቶች ሊያገረሹ የሚችሉበት ሁኔታ እንዳለ ተጠቁሟል፡፡
ደህንነታቸው ፍፁም የተጠበቀ አይደለም ተብለው በ4ኛ ደረጃ ከተመደቡት መካከል ደግሞ የሶማሌ ክልል ተጠቃሽ ነው፡፡ የጉዞ ማስጠንቀቂያው በ4ኛ ደረጃ ወደተመደቡ አካባቢዎች የሚደረግን ጉዞ ይከለክላል፡፡
ሁኔታዎች በተሻሻሉ ቁጥር በሪፖርቱ ላይ ማስተካከያዎች እንደሚደረጉ የአሜሪካ የውጭ ጉዳይ መስሪያ ቤት አስታውቋል፡፡

የህዝብ ተወካዮች ም/ቤት ከ4 ዓመት በላይ አነጋጋሪና አከራካሪ ሆኖ በቆየው የውጭ ሃገር የህፃናት ጉዲፈቻ ጉዳይ ላይ ውሳኔ ያሳለፈ ሲሆን ህፃናት በጉዲፈቻ ለውጭ ሀገራት ዜጎች እንዳይሰጡ የሚከለክለውን አዋጅ ሰሞኑን አፅድቋል፡፡
የምክር ቤቱን ውሳኔ ተከትሎ ቢቢሲ እና ዘ ጋርዲያንን ጨምሮ በርካታ አለማቀፍ መገናኛ ብዙኃን ጉዳዩን ሁነኛ መነጋገሪያ ያደረጉት ሲሆን የኢትዮጵያ መንግስት ከዚህ ውሳኔ ላይ ያደረሰው እ.ኤ.አ በ2013 አሜሪካዊያን ጥንዶች ለማሳደግ የወሰዷትን ህፃን፣ በጭካኔ ከገደሉ በኋላ በተፈጠረ ቁጣ ነው ብለዋል፡፡
ሰሞኑን በህዝብ ተወካዮች ም/ቤት የፀደቀው አዋጁ፤ ህፃናትን ከእንግዲህ ለውጭ ሀገር ዜጎች በማደጎነት መስጠት እንደማይቻል የሚደነግግ ሲሆን ህጉን በሚጥሱት ላይ  ቅጣት ማስቀመጡም ታውቋል፡፡
ይህን አዋጅ ለመደንገግ ያስፈለገበት ምክንያት በማደጎነት ለውጭ ሀገር እየተሰጡ ባሉ ህፃናት ላይ የሚደርሱ ኢ-ሰብአዊ ድርጊቶች እየተባባሱ በመምጣታቸው መሆኑም ተመልክቷል፡፡
ከእንግዲህ ሁሉም ኢትዮጵያውያን ህፃናት በተወለዱበት ሀገር ቋንቋውን፣ ባህሉን እየተማሩ ብቻ ነው ማደግ የሚችሉት የተባለ ሲሆን ወላጅ አልባ ህፃናትም በሃገር ውስጥ የማሳደጊያ ማዕከል የሚያድጉበት እድል እንደሚፈጠር ተጠቁሟል፡፡ የሃገር ውስጥ የጉዲፈቻ ባህልም እንዲስፋፋ ይደረጋል ተብሏል፡፡
በአዋጁ ላይ ሰፊ ሃተታ ያቀረቡት ቢቢሲ እና ፎክስ ኒውስ፤ ኢትዮጵያውያን ህፃናትን በማደጎነት በመውሰድ ጉልህ ድርሻ ባላት አሜሪካ ዘንድ ውሳኔው ቅሬታ መፍጠሩን ጠቁመዋል፡፡ የማደጎ ልጆችን ከሚያሳድጉ አሜሪካውያን መካከል 20 በመቶ የሚሆኑት ኢትዮጵያውያን ልጆች እንዳሏቸው የተመለከተ ሲሆን እ.ኤ.አ. ከ1999 እስከ 2017 ባሉት 18 ዓመታት ውስጥ ከ15 ሺህ በላይ ኢትዮጵያውያን ህጻናት  በማደጎነት ወደ አሜሪካ ተወስደዋል፡፡ ቁጥራቸው በውል ያልታወቁ ህጻናት ደግሞ በዋናነት ወደ ስፔን፣ ፈረንሳይና ጣሊያን በማደጎነት ሲወሰዱ ነበር ተብሏል፡፡ ኢትዮጵያ ህፃናትን ለውጭ አገራት ዜጎች በማደጎነት በመስጠት ከሚታወቁ  አስር የዓለም አገሮች አንዷ እንደነበረችም መረጃዎች ይጠቁማሉ፡፡   

    - የቀድሞው መሪ ሳኒ አባቻ 4 ቢ. ዶላር ያህል መዝረፋቸው ተነግሯል

    የቀድሞው የናይጀሪያ ፕሬዚዳንት ሳኒ አባቻ ዘርፈውታል የተባለውና የሙስና ምርመራ ለማድረግ በአሜሪካ የተያዘው ግማሽ ቢሊዮን ዶላር እንዲመለስ፣ የናይጀሪያ ኢኮኖሚያዊና ማህበራዊ መብቶች የተባለው የአገሪቱ የመብቶች ተከራካሪ ቡድን ለትራምፕ አስተዳደር ጥያቄ አቅርቧል፡፡ የቀድሞው የናይጀሪያ ፕሬዚዳንት ሳኒ አባቻ፣ በስልጣን ዘመናቸው በድምሩ 4 ቢሊዮን ዶላር ያህል የህዝብ ሃብት መዝብረዋል መባላቸውን ያስታወሰው የሲኤንኤን ዘገባ፤ቡድኑም ከዚህ ገንዘብ ውስጥ በአሜሪካ እጅ ውስጥ ግማሽ ቢሊዮን ዶላር እንደሚገኝና ገንዘቡ ለህዝቡ እንዲመልስ ለትራምፕ አስተዳደር በደብዳቤ መጠየቁን አመልክቷል፡፡ ናይጀሪያ በኢኮኖሚ መቀዛቀዝ ላይ ባለችበት በዚህ ወሳኝ ወቅት በአሜሪካ እጅ ላይ የሚገኘው የህዝብ ገንዘብ በአፋጣኝ መመለሱ አግባብ ነው፤ ትራምፕ ገንዘቡን ይመልሱና ህዝቡን ተጠቃሚ በሚያደርጉ ስራዎች ላይ ይዋል ብሏል፤ ቡድኑ ባወጣው መግለጫ፡፡
የናይጀሪያው ፕሬዚደንት መሃመድ ቡሃሪ ከቀድሞው የአሜሪካ ፕሬዚዳንት ባራክ ኦባማ ጋር በጉዳዩ ዙሪያ መወያየታቸውንና ገንዘቡን ለመመለስ መስማማታቸውን ያስታወሰው ዘገባው፤ በአንዳንድ ቢሮክራሲያዊ አሰራሮች ምክንያት ገንዘቡ ሳይመለስ የትራምፕ አስተዳደር ወደ ስልጣን መምጣቱን አስረድቷል፡፡እ.ኤ.አ በ1998 ከዚህ አለም በሞት የተለዩት የቀድሞው የናይጀሪያ ፕሬዚዳንት ሳኒ ኣባቻ፣ በተለያዩ አገራት የነበሯቸው ገንዘቦችና ንብረቶች እንዳይንቀሳቀሱ መታገዱን ያስታወሰው ዘገባው፤ ስዊዘርላንድ 700 ሚሊዮን ዶላር ያህል ገንዘብ ለናይጀሪያ መንግስት መመለሷን ገልጧል፡፡

    አገሪቱ በ2016 ካደረገቻቸው 6 የሚሳኤል ሙከራዎች 3ቱ ከሽፈዋል

    ነጋ ጠባ ሚሳኤል እያስወነጨፈች የጎረቤቶቿንና የተቀረውን አለም ቀልብ በመግፈፍ ላይ የምትገኘው ሰሜን ኮርያ ባለፈው ሚያዝያ ወር ላይ ለሙከራ ያስወነጨፈቺው ባለስቲክ ሚሳኤል መክሸፉና ከመዲናዋ ፒንግያንግ በቅርብ ርቀት ላይ የሚገኝ ከተማን መደብደቡ መረጋገጡን  ኒውዮርክ ፖስት ዘግቧል፡፡
ሰሜን ኮርያ ባለፈው አመት ካደረገቻቸው ስድስት የሚሳኤል ሙከራዎች ሶስቱ መክሸፋቸውን ያስታወሰው ዘገባው፤በሚያዝያ ወር መጨረሻ ላይ ያስወነጨፈቺው ሃዋሶንግ 12 የተሰኘ ባለስቲክ ሚሳኤል ለአንድ ደቂቃ ያህል ከተጓዘ በኋላ በመክሸፍ ተመልሶ ቁልቁል ወርዶ፣ ቶክቹን የተባለቺውን የአገሪቱ ከተማ ማጥቃቱን አመልክቷል፡፡ ይሄው መካከለኛ ርቀት ተወንጫፊ ባለስቲክ ሚሳኤል ፑክቻንግ ከተባለው የአገሪቱ የማስወንጨፊያ ተቋም ከተተኮሰ በኋላ ባጋጠመው የቴክኒክ ችግር ምክንያት ሞተሩ መበላሸቱንና ወደ መሬት ተመልሶ በቶክቹን ከተማ ይገኙ የነበሩ የኢንዱስትሪና የግብርና መሰረተ ልማቶችን ማውደሙን አንድ የአሜሪካ መንግስት ባለስልጣን በምርመራ አረጋግጠናል ማለታቸውን ዘገባው አስረድቷል፡፡
የከሸፈው ሚሳኤል ያደረሰውን ሰብዓዊ ጉዳትና ዝርዝር ጥፋት ለማወቅ ባይቻልም በሳተላይት የተነሱ ምስሎች ግን ከፍተኛ ጥፋት ማድረሱን እንደሚያመልክቱ የጠቆመው ዘገባው፤ የሚሳኤሉ መክሸፍ ከዚህ ቀደም በወሬ ደረጃ ቢነገርም በተጨባጭ ተረጋግጧል የሚል ዘገባ ሲወጣ ግን ይህ የመጀመሪያው መሆኑንም አክሎ ገልጧል፡፡

  የህንዱ ታጅ ማሃል በእረፍት ቀናት እስከ 70 ሺህ ቱሪስቶች ይጎበኙታል

    የህንድ መንግስት በ17ኛው መቶ ክፍለ ዘመን እንደተገነባ የሚነገርለትንና ከአለማችን ጥንታዊ የቱሪዝም መስህቦች አንዱ የሆነውን ታጅ መሃልን፣ በአንድ ቀን ውስጥ መጎብኘት የሚችሉ የአገሪቱ ቱሪስቶች ቁጥር ከ40 ሺህ በላይ እንዳያልፍ የሚያስገድድ ህግ ተግባራዊ ሊያደርግ ማቀዱ ተዘግቧል፡፡
ታጅ ማሃል በተለይ በእረፍት ቀናት እስከ 70 ሺህ በሚደርሱ ህንዳውያን እንደሚጎበኝ ያስታወሰው ቢቢሲ፤፣ ከቱሪስቶች መብዛት ጋር በተያያዘ በጥንታዊው የቱሪስት መስህብ ላይ ጥፋቶች እየደረሱ በመሆኑ ይህንን ጥፋት ለመቀነስ በማሰብ መንግስት በአንድ ቀን ውስጥ ከ40 ሺህ በላይ የአገር ውስጥ ቱሪስት እንዳይጎበኘው ለማገድ ማቀዱን ዘግቧል፡፡ በቅርቡ ተግባራዊ ይደረጋል ተብሎ የሚጠበቀው ይህ ህግ፣ ህንዳውያን ቱሪስቶች በዩኔስኮ የአለም ቅርስነት በተመዘገበው ታጅ ማሃል የሚኖራቸውን የጉብኝት ቆይታ ጊዜ 3 ሰዓታት ብቻ እንደሚያደርገውም ዘገባው አመልክቷል፡፡
አዲሱ የታጅ መሃል ህግ በህንዳውያን ቱሪስቶች ላይ እንጂ በሌሎች አገራት ጎብኝዎች ላይ እንደማይሰራ መነገሩን የጠቆመው ዘገባው፣ ታጅ ማሃል በ2016 የፈረንጆች አመት ብቻ ከአገር ውስጥና ከውጭ አገራት ጎብኝዎች 8.8 ሚሊዮን ፓውንድ ያህል ገቢ ማስገኘቱን አስታውሷል፡፡

--------------------------


               ሙጋቤ ቤትና 3 ዘመናዊ መኪኖችን ጨምሮ ጠቀም ያለ ጡረታ ይሰጣቸዋል

   አዲሱ የዚምባበዌ መንግስት ለቀድሞው የአገሪቱ ፕሬዚዳንት ሮበርት ሙጋቤ ዳጎስ ያለ ደመወዝ፣ ምቹ የመኖሪያ ቤትና ሶስት ዘመናዊ መኪኖችን ጨምሮ ተገቢውን የጡረታ ጥቅማጥቅም እንዲከበርላቸው ውሳኔ ማሳለፉን ዘ ቴሌግራፍ ዘግቧል፡፡
አገሪቱን ለ37 አመታት ያህል የገዙትና በቅርቡ ስልጣናቸውን የለቀቁት ሙጋቤ፣ ጠባቂዎችን ጨምሮ በእለት ተእለት እንቅስቃሴያቸው “አቤት ወዴት” ብለው የሚታዘዟቸው 20 ሰራተኞች ይመደቡላቸዋል ያለው ዘገባው፤ በአመት አራት ነጻ የአንደኛ ደረጃ የአውሮፕላን በረራ አገልግሎትና ሌሎች ጥቅማ ጥቅሞችንም እንደሚያገኙ አመልክቷል፡፡
ሙጋቤ የጡረታ ህይወታቸውን በምቾት ያሳልፉ ዘንድ ከአዲሱ መንግስት ዘመናዊ መርሴድስ ቤንዝን ጨምሮ ሶስት መኪኖች እንደሚሰጧቸው የጠቆመው ዘገባው፤ ዕድሜ ይስጣቸው እንጂ በህይወት እስካሉ ድረስ የሶስቱንም መኪኖች የነዳጅ ወጪ የሚሸፍንላቸውም የአገሪቱ መንግስት ነው መባሉን ገልጧል፡፡
ሙጋቤ ከአዲሱ መንግስት የገንዘብ ድጎማ ይደረግላቸው አይደረግላቸው የታወቀ ነገር የለም ያለው ዘገባው፣ ይህም ሆኖ ግን አንዳንድ መገናኛ ብዙሃን ሙጋቤ ስልጣናቸውን የለቀቁት 10 ሚሊዮን ዶላር እንደሚሰጣቸው ቃል ተገብቶላቸው ነበር ሲሉ መዘገባቸውን አስረድቷል፡፡
መገናኛ ብዙሃኑ ከዚህ በተጨማሪም ሙጋቤ ስልጣናቸውን በፈቃዳቸው የሚለቁ ከሆነ በራሳቸው መሬት ላይ ዘመናዊ መኖሪያ ቤት እንደሚገነባላቸውና ጥበቃዎችን ጨምሮ ሙሉ ሰራተኞች እንደሚቀጠሩላቸው ተነግሯቸው ነበር ማለታቸውንም ዘገባው አስታውሷል።

 • ጃፓን በታሪኳ ከፍተኛውን የ46 ቢ. ዶላር ወታደራዊ በጀት አጽድቃለች

    የሰሜን ኮርያ ጸብ አጫሪነት ጃፓንን ከ2ኛው የዓለም ጦርነት ወዲህ በታሪኳ አይታው የማታውቀው እጅግ የከፋ የደህንነት አደጋና ስጋት እንደጋረጠባት የገለጹት የአገሪቱ ጠቅላይ ሚኒስትር ሺንዞ አቤ፤ዜጎችን ከጥፋት ለማዳን ሲሉ የጦር ሃይላቸውን በተለየ ሁኔታ እንደሚያጠናክሩ አስታውቀዋል፡፡
“እየተባባሰ የመጣው የሰሜን ኮርያ ጦር ናፋቂነት፣ አገሬን ከሁለተኛው የዓለም ጦርነት ወዲህ አይታው በማታውቀው እጅግ የከፋ የደህንነት ስጋት ውስጥ ከትቷት ይገኛል፤ የህዝቤን ህይወትና ሰላማዊ ኑሮ ከሰሜን ኮርያ ሊቃጣ ከሚችል ጥቃት ለመታደግ ከመቼውም ጊዜ በበለጠ በጽናት እቆማለሁ!” ብለዋል ጠቅላይ ሚኒስትር አቤ ከትናንት በስቲያ በሰጡት ጋዜጣዊ መግለጫ - ሮይተርስ እንደዘገበው፡፡
ሰሜን ኮርያ፤ ጃፓንና አለማቀፉ ማህበረሰብ የያዘውን የሰላማዊ መንገድ አቅጣጫ እያሰናከለችና በጸብ አጫሪነት አመሏ አካባቢውን ውጥረት ውስጥ እየከተተች መቀጠል አትችልም ያሉት ጠቅላይ ሚኒስትሩ፤ ጃፓን የሰሜን ኮርያን ጥቃት ለመከላከል የጦር ሃይሏን ከመቼውም ጊዜ በተለየ እንደምታጠናክር መናገራቸውን ዘገባው አመልክቷል፡፡
የአካባቢው አገራት በሰሜን ኮርያ እምቢተኝነትና ጦር ጠማኝ አቋም ሳቢያ የገቡበት ውጥረት እየተባባሰ መምጣቱ ያሳሰበው የጃፓን መንግስት፤ባለፈው ወር ላይ ለጦር ሃይሉ 46 ቢሊዮን ዶላር አመታዊ ወታደራዊ በጀት ማጽደቁንና ይህም በአገሪቱ ታሪከ ከፍተኛው እንደሆነም ዘገባው አክሎ ገልጧል፡፡
የተመድ ማዕቀብና አለማቀፉ ማህበረሰብ ማስጠንቀቂያ ቅንጣት ታህል ድንጋጤ ያልፈጠረባት ሰሜን ኮርያ፤፣  በተለይም ባለፈው መስከረም ወር ላይ ስድስተኛውንና ትልቁን የሚሳኤል ሙከራ ማድረጓንና በህዳር ወርም አሜሪካን መምታት የሚችል የረጅም ርቀት ድንበር ተሸጋሪ ባለስቲክ ሚሳኤል ሙከራ በተሳካ ሁኔታ ማከናወኗን በይፋ ማስታወቋን ተከትሎ በአካባቢው አገራት የነበው ውጥረት በከፍተኛ ሁኔታ መባባሱንም ዘገባው አስታውሷል፡፡

  ሞርኒንግ ስታር ሞል - የገና ልዩ ቅናሽ

    ቦሌ ኤድናሞል ጎን የሚገኘውና አገልግሎት መስጠት ከጀመረ ከ3 ዓመት በላይ የሆነው ሞርኒንግ ስታር ሞል፤ ከባለፈው ሰኞ ጀምሮ የጌታን ልደት ለማስታወስ በአይነቱ ልዩ የሆነና 20 ሜትር ርዝመት ያለው የገና ዛፍ ሰርቶ በሩ ላይ አቁሟል። ይህ ግዙፍ የገበያ ማዕከል ከዛፉ በተጨማሪ ጌታ የተወለደበትን ቦታ ለማስታወስም በረት የሰራ ሲሆን ከማዕከሉ ፊት ለፊት የኢትዮጵያ ቡና አፈላል ሥነ - ስርዓት የሚካሄድበት ዳስ ጥሎ፣ ሰዎች ቡና እየጠጡ የሚፈልጉትን እቃ ለገና በዓል በተደረገ ልዩ ቅናሽ እየሸመቱ፣ የሚዝናኑበትን  ሁኔታ አመቻችቷል፡፡
ይህ ግዙፍና 20 ሜትር ርዝመት ያለው ዛፍ፣ የፈረንጆቹንም የሀበሻንም የገና ዛፍ አሰራር ያጣመረና አካባቢን በማያቆሽሽ መልኩ የተሰራ ሲሆን በአጠቃላይ 60 ሺህ ብር መፍጀቱን የሞርኒንግ ስታር ሞል የማርኬቲንግ ባለሙያ አቶ ሳሙኤል ሙሉጌታ ጠቁመው፣ እስከ ዛሬ ምሽት በሚቆየው ልዩ ዝግጅት፤ ሰዎች እንዲታደሙ ጥሪ አቅርበዋል፡፡

----------------------


           ኢሊሌ ኢንተርናሽናል - ቪአይፒ ሬስቶራንት

   ባለ አምስት ኮከቡ ኢሊሌ ኢንተርናሽናል ሆቴልም እንደዚሁ ልዩ የገና የእራት ምሽት፣ 10ኛ ፎቅ ላይ በሚገኘው እጅግ ምቹና ዘመናዊ በሆነው ቪአይፒ ሬስቶራንቱ አዘጋጅቷል፡፡
“ዴሉክስ ሜኑ” የተባለው ልዩ እራት በምቹው ሬስቶራንት ውስጥ በለስላሳ ሙዚቃ ታጅበው፣ ከወይን መጠጥና ቢራ ጋር የሚያጣጥሙበት ልዩ ምሽት መሆኑን የሆቴሉ የህዝብ ግንኙነት አቶ ታሪኩ ዋስይሁን ተናግረዋል፡፡ ከምሽት 12፡00 እስከ እኩለ ሌሊት በሚዘልቀው በዚህ የእራት ምሽት ላይ ለመታደም ለአንድ ሰው 700 ብር፣ ለጥንዶች 1400 ብር ክፍያ እንዳለውም አቶ ታሪኩ ጨምረው ገልፀዋል፡፡


---------------


                ኢንተርኮንትኔንታል - እራትና ሙዚቃ በባንድ

   ባለ አራት ኮከቡ ኢንተርኮንትኔንታል ሆቴል፣ 11ኛ ፎቅ ላይ በሚገኘውና አዲስ ባሰራው ተሽከርካሪ ሬስቶራንቱ ልዩ የገና እራትና በባንድ ቀጥታ የሚተላለፍ የሙዚቃ ዝግጅት አሰናድቷል። ዛሬ በበዓሉ ዋዜማ ከምሽቱ 12፡00 እስከ እኩለ ሌሊት በሚዘልቀው በዚህ የመዝናኛ መሰናዶ፤ በተለይ በገና ወቅት በብዛት የሚበሉት ተርኪ፣ ቺክንና መሰል ምግቦች በልዩ ሁኔታ ተከሽነው የሚቀርቡ ሲሆን እንግዶች ያሻቸውን መጠጥ መጠቀም እንደሚችሉም ተገልጿል፡፡ በዚህ ምሽት  እራት ለመመገብ 760 ብር የሚያስከፍል ሲሆን አስርና ከዚያ በላይ በቡድን ለሚመጡ የ10 በመቶ ቅናሽ እንደሚደረግላቸው የሆቴሉ የሽያጭና ገበያ ዳይሬክተር አቶ ወገኔ ታደሰ ገልፀዋል፡፡
በተጨማሪም በሆቴሉ  የሚገኘው ቮልቴጅ ክለብ፣ ከምሽቱ 3፡00 ጀምሮ ልዩ የገና የዲጄ ሙዚቃ መዘጋጀቱን የገለጹት ዳይሬክተሩ፤ መግቢያው ነፃ እንደሆነና እስከ ሌሊቱ 9፡00 እንደሚዘልቅ ተናግረዋል፡፡


---------------


                   ራማዳ አዲስ- ልዩ እራት

   ከአንድ ዓመት ተኩል በፊት በመሃል ቦሌ ከአገልግሎት መስጠት የጀመረው ባለ 4 ኮከቡ ራማዳ አዲስ ሆቴል ለገና ዋዜማ “ሼፍስ ክለብ” እና “ፎጎ ኖቾ” በተባሉት ሁለት ታዋቂ ሬስቶራንቶች ውስጥ ልዩ የእራት ምሽት አዘጋጅቷል፡፡
በዚህ ልዩ የእራት ምሽት “ኢትዮ ኳርቴት” የተባለ የሙዚቃ ባንድ ልዩ የሙዚቃ ትርኢት በቀጥታ ለታዳሚው እንደሚያቀርቡም የሆቴሉ ፀሀፊ አቶ የኔአለም ክፍሉ አስታውቀዋል፡፡


-----------------

           በብሔራዊ ቴአትር - ልዩ ሙዚቃ

    ታላቁ ብሔራዊ ቴአትር በገና በዓል ዕለት እሁድ ከሰዓት በኋላ ከቀኑ 8፡00 ጀምሮ ልዩ የሙዚቃ ዝግጅት ያቀርባል፡፡
ባህላዊና ዘመናዊ ሙዚቃዎች በልዩ ሁኔታ በሚቀርቡበት በዚህ የበዓል የሙዚቃ ዝግጅት የቴአትር ቤቱ አንጋፋና ወጣት ድምፃዊያን “ቫራይቲ” በተሰኘው የቴአትር ቤቱ ኦርኬስትራ ታጅበው፣ ታዳሚውን እንደሚያዝናኑ የታወቀ ሲሆን የባህል ሙዚቃ ኦርኬስትራውም ከባህላዊ ሙዚቃ ድምፃውያን ጋር ሆኖ በዓሉን በዓል እንደሚያስመስሉት የቴአትር ቤቱ የሙዚቃ ዳይሬክቶሬት ዳይሬክተር አቶ ወሰን የለህ መብረቁ ለአዲስ አድማስ ተናግረዋል፡፡
እስከ ቀኑ 11፡00 በሚዘልቀው የበዓል ልዩ የሙዚቃ ዝግጅት ላይ ለመታደም  መግቢያው 40 ብር እንደሆነ ታውቋል፡፡

----------------------


              “ሃፒ ኢቨንትስ” ልዩ የገና ዋዜማ ጨዋታዎችን አዘጋጅቷል

              “ለልጆች የደስታ ቀን ለመፍጠር የታሰበ ነው”
                 ግሩም ሠይፉ

    “ሃፒ ኢቨንትስ” አዳዲስና የተለያዩ የገና ዋዜማ ጨዋታዎችን ለልጆች ማዘጋጀቱን አስታወቀ፡፡ የዋዜማ ዝግጅቱ  ቦሌ ድልድይ አካባቢ ከቦራ መዝናኛ ማዕከል አቅራቢያ በሚገኘው በቦሌ ህብረተሰብ 1ኛ ደረጃ ትምህርት ቤት ቅጥር ግቢ ውስጥ ዛሬ ከጠዋቱ 3 ሰዓት ጀምሮ እስከ 8 ሰዓት የሚካሄድ ሲሆን መግቢያው ለህፃናት 100 ብር፣ ለወላጆች በነፃ መሆኑ ታውቋል፡፡
 አዘጋጆቹ ልዩ የገና ዋዜማ ጨዋታዎችና መዝናኛዎችን ያሰናዱበትን ምክንያት ለአዲስ አድማስ ሲገልፁ፤ከፈተና መልስ ለልጆች የገናን በዓል ምክንያት በማድረግ  የደስታ ቀን ለመፍጠር በማሰብ ነው ብለዋል፡፡
የ”ሃፒ ኢቨንትስ” ሁለት አርቲስቶች የሻማ ቀራፂና ሰዓሊ አስናቀ ክፍሌ እና ሳሮን ከፍአለ ሲሆኑ አብሯቸው የሚሰራው ደግሞ የህፃናት አጫዋችና የሰርከስ ባለሙያ የሆነው ተመስገን ግርማ ነው፡፡ አርቲስት አስናቀና  ሳሮን ለህፃናት በአዲስ መልክ የፈጠሯቸውንና ከሌሎች አገራት በመመልከት በሰሯቸው ልዩ ልዩ ጨዋታዎችና ውድድሮች ህፃናትን የሚያዝናኑ ሲሆን መዝለያዎች ፤ የቅርጫት ኳስ፤ ቀለም መቀባት፤ የህፃናት ፎቶ፤የፊት ላይ ስዕሎች፤ የህፃናት አዝናኝ ትረካና ሌሎች የተለያዩ መዝናኛዎችን እንደሚያቀርቡ ለማወቅ ተችሏል፡፡
በበርካታ ህጻናት ዘንድ “ጥሩንቤ” በሚለው ስሙ የሚታወቀው ተመስገን ግርማ፤ከቅርብ ጊዜያት ወዲህ በሳሙና አረፋዎች በሚሰራቸው  አስደናቂ ትርኢቶች አድናቆትን ያተረፈ ሲሆን በዛሬው ዕለት ህጻናትን ለማዝናናት ዝግጁ ሆኖ ይጠብቃል ተብሏል፡፡