Administrator

Administrator

ላለፉት 50 ዓመታት በፎቶግራፍ ባለሙያነት የሰሩትና ባለፈው መስከረም 6 ቀን 2009 ዓ.ም በድንገተኛ ህመም ሀይወታቸው ያለፈው አቶ ተሾመ ንጉሴ ነገ ከቀኑ 10፡00 ጀምሮ በአዳማ ኩሪፍቱ ሪዞርት በተለያዩ ዝግጅቶች እንደሚዘከሩ የፕሮግራሙ አስተባባሪዎች ለአዲስ አድማስ ገለፁ፡፡ በዕለቱ የህይወት ታሪካቸውን የሚያስቃኝ ዘጋቢ ፊልም ግጥምና የህይወት ታሪካቸው የሚቀርብ ሲሆን የፎቶግራፍ ስራዎቻቸውን ለእይታ በማቅረብም እንደሚዘከሩ ለማወቅ ተችሏል፡፡

Sunday, 26 February 2017 00:00

ገቢና ወጪ - (ወግ)

  “መቼም ያለ ፈጣሪ መኖር የማይሆንልን ከሆነ … መቼስ ምን ማድረግ ይቻላል?” ብሎ ዝም አለ፤ የክሪስቶፈር ሂችንስን መፅሐፍ ከአዛውንቱ ተውሶ ሲያነብ የቆየው ወጣት፡፡ መፅሐፉን በእጁ ላይ ይዞ እየደባበሰው ነው፡፡
አዛውንቱ ወፍራሙን ጋቢያቸውን ለብሰው፣ በቀዝቃዛው የክረምት ጭጋግ ውስጥ ቆመዋል፡፡ ወጣቱ በአዛውንቱ ግቢ ውስጥ ከጎናቸው ቆሟል። እጁን በአክብሮት ከጀርባው አጣምሮታል፡፡ በእጁ ላይ መፅሐፉን ይዞ ይደባብሰዋል፡፡ አዛውንቱ ነባር ሳይንቲስትና ኢ-አማኒ ናቸው፡፡ ኢ -አማኒ ናቸው ይባልላቸዋል እንጂ የሚያምኑት የሌላቸው አይደሉም፡፡ ለምሳሌ በህይወት ያምናሉ፡፡ ባያምኑ እስከዚህ እድሜ ድረስ መኖር አይችሉም ነበር … ብሎ አሰበ ወጣቱ፤መፅሐፉን እየደባበሰ፡፡
“ያለ ፈጣሪ መኖር የማይሆንልን ከሆነ፣ የሚመጥነንን ፈጣሪ መፍጠር ነዋ!” አሉ አዛውንቱ። አፍንጫቸውን የማሸት ባህርይ አላቸው፡፡ በመደባበስ ብዛት መፅሐፉ በወጣቱ እጅ ላይ እንዳረጀው .. የአዛውንቱ አፍንጫ ደግሞ ከሌላው የፊታቸው ቅላት ተለይቶ ጠቁሯል፡፡
“ፈጣሪ ባይኖር ኖሮ ልንፈጥረው እንገደድ ነበር ---- እንዳለው ማለትዎ ነው?” አለ ወጣቱ፤ ከእርስዎ ባላውቅም በሚል ትህትና፡፡
“አዎ በትክክል … ግን ቮልቴር መፍጠር ያለብን ምን አይነቱን ፈጣሪ ነው ብትለው መልስ የለውም … እኔ ደግሞ የምለው መፍጠር የማትችለውን ፈጣሪ ለምን ወደዛ አትተወውም … ከአቅምህ በላይ ከሆነ … መተው አይሻልም?!” ብለው አፍንጫቸውን መፈተግ ቀጠሉ፡፡ ጣታቸው በአፍንጫቸው ቀዳዳ ገብቶም እንደማፅዳት ይልና፣ ከዛ ደግሞ ወደ ላይና ወደ ታች እየተመላለሰ መፈተጉን ይቀጥላል። የማሰላሰያ ጊዜ ለመግዛት የሚያደርጉት ሙከራ ሳይሆን አይቀርም ብሎ ወጣቱ ጠረጠረ፡፡ እሱም የራሱ የማሰላሰያ ቴክኒክ አለው፡፡ በልማድ ሁለት እጆቹን እያጨባበጠ መፈተግ ይቀናዋል፡፡ አሁን በእጆቹ መሀል ያለው መፅሐፍ ስለሆነ፣ የመፅሐፉ ገፆች ወደ መላላጥ ቀርበዋል፡፡
ወሬውን ወደ ሌላ አቅጣጫ ለመቀየር “ዛሬ ልደቴ ስለሆነ አንዳች ነገር ማድረግ አሰኝቶኛል” አለ ወጣቱ፤ መፅሐፉን ለአዛውንቱ እያቀበላቸው። ለመቀበል ፍላጎት ያላቸው አልመሰሉም፡፡ የተዘረጋው እጁ ተንከርፍፎ በአየር ላይ ቀረ፡፡
“ስንተኛ ዓመት ልደትህ ነው? … የሚገርም ነው፤ እኔ በአንተ እድሜ ሳለሁ ስለልደቴ ምንም አላውቅም ነበር፡፡ ለመወለድና ለልደት ቀን ከፍ ያለ ግምት እንዲኖር፣ የኑሮ ደረጃም ከፍ ማለት አለበት። … እኔ ወጣት ሳለሁ ዋነኛው ነገር ሚስት አግብቼ፣ ልጆች ወልዶ ማስተማር ነበር ቁም ነገሩ” ብለው ድንገት ዝም አሉ፡፡ ወደ ትዝታ፣ ወደ ኋላ ዘመን ሲሸመጥጡ … አፍንጫቸውን ተወት አደረጉት፡፡ ሀሳብ ከአፍንጫ ጋር ያለው ትስስር ጠንካራ መሆኑ ወጣቱን በድጋሚ ተሰማው፡፡
“አሁን አንተ የምታነበውን አይነት መፅሐፍ፣ እኔ ወጣት በነበርኩበት ጊዜ የማንበብ ፍላጎት አልነበረኝም፡፡ በዛ ዘመን የማምንበት ፈጣሪ መጠኔ ስለመሆኑ እርግጠኛ ነበርኩኝ፡፡ ፈጣሪና እኔ ተስማምተን ነበር የምንኖረው፡፡ ከመስማማታችንም በላይ በጥልቅ የምንነጋገር፣ የምንቀራረብ ይመስለኝ ነበር፡፡ ታውቃለህ አይደል፤ መስማማት ማለት ባለህበት መርገጥ ማለት ነው፡፡ … እኔና ፈጣሪዬ ባለንበት ብንረግጥም … ተፈጥሮና የህይወት ሂደት ግን ይለወጣል፡፡ … ለውጥ መጣ፡፡ የተማሪዎች እንቅስቃሴ ይዞ የመጣው ሀሊዮ፣ በእኔና በፈጣሪ መሀል አለመግባባትን ፈጠረ፡፡ የፈጣሪ ንግግር ለሚያድገው አእምሮዬ ጠበበኝ፡፡ ልክ የልጅነቴን ልብስ በሚያድገው አካላቴ ላይ አምጥተው እንዳጠቀለቁልኝ ጠበበኝ፤ … ጥበቱን ለማስፋት አንድም የበለጠ ሀይማኖተኛ መሆን አልያም … የጭንቅላቴን መጠን አስፍቼ የበለጠ ማሰብና ማወቅ ነበር ያለኝ አማራጭ፡፡ ከዚህ በላይ አማራጭ መኖሩን ለማወቅ ራሱ ማወቅና የአስተሳሰብን አድማስ ማስፋት … ቀዳሚ ግዴታዬ ነበር ..” … ብለው እንደገና ወሬያቸውን አቋረጡ፡፡
ወጣቱ አንዳች ነገር ጠረጠረ፡፡ አዛውንቱ የሆነ ማስረጃ ለማቅረብ እየሞከሩ እንደሆነና … ከጥንቱ ፈጣሪያቸው ጋር የነበራቸው መግባባትና ቅርርብ እንደገና እየናፈቃቸው እንደሆነ ጠረጠረ፡፡ ዝም ብሎ ማድመጡን ቀጠለ፡፡ በመሀል ቀስቃሽ ጥያቄዎችን ይሰነዝርላቸዋል፡፡
“እርስዎ የሚያምኑት ፈጣሪ፣ በምን ሀይማኖት ውስጥ የሚገኝ ነበር?”
“እምነት በመሰረቱ እንደ ባህል ከአፈራህ ማህበረሰብ የምትወርሰው ነው፣ መጀመሪያ፡፡ ዝግ ማህበረሰብ ውስጥ ያለ ፈጣሪና የሰለጠነ ወይንም ሰፊ አመለካከትን ያዳበረ ማህበረሰብ ያለው ፈጣሪ ይለያያል፡፡ … ግን መለያየቱ … ሔዶ የሚገናኝበት ቦታ ይኖረዋል፡፡ ሁሉም ፈጣሪን በሰው አምሳል … ወይንም ለሰው የተሳለ ማድረጋቸው ላይ ዞረው ዞረው ይግባባሉ፡፡ … ስለዚህ ፈጣሪ ራሱ የሚኖረው ገፅታ እንደ ሰው ገፅታ ከመሆን አይወጣም፡፡ ልክ ፈረንጅ ሰውና በአፍሪካ ጫካ ያለ የቡሽሜን ኋላ ቀር ሰው .. ሆነም ቀረ ሰው መሆናቸው ላይ እንደሚስማሙት ይሆናል፤ፈጣሪም … እና ምን ለማለት ፈልጌ ነው … ሰው ራሱን ከሰው በላይ አድርጎ ካልፈጠረ … ፈጣሪውም ከሰውኛ ባህርይ የተላቀቀ ሊሆን አይችልም፡፡”
“በእጅ አዙር የተነሳንበትን ጥያቄ መለሱልኝ። መፍጠር ያለብን ሰውን ነው ማለታቸው ነው፡፡ ሰውን አንድ ማድረግ እስካልተቻለ፣ፈጣሪም ይህንኑ የሚከተል ነው፡፡ …. ከባህላዊው እስከ ዘመናዊው …. ከጨካኙ እስከ ክርስቶሳዊው፣ ትሁት ፈጣሪ ያሉት ሀይማኖታዊ ትርክቶች … ስለ ፈጣሪ ከሚነግሩን ይልቅ ስለ ሰው ልዩነት የሚነግሩን መረጃ የበለጠ ነው፡፡”
“ስለ እድሜ ሊነግሩኝ የሚፈልጉት ነገር ነበር ልበል?” እያለ ወጣቱ በግድ መፅሐፉን አስጨበጣቸው፡፡ መቀበል የፈለጉ ግን አይመስሉም። … መፅሐፉ ውስጥ ያለውን አስተሳሰብ አልፈውት የሄዱ መሰለው፡፡ አልፈው ሄደው የት እንደደረሱ ግን እርግጠኛ አልነበረም፡፡ የደረሱበት ቦታ ከጠፋቸው ደግሞ አደገኛ ነው፡፡ በጠፋው መልስ ፋንታ ትዝታ በክፍተቱ መሀል ይገባል፡፡ የጥንቱ የፈጣሪ ዕምነት ከብዙ ጥንታዊ የልጅነት ትዝታ ጋር የተሳሰረ ስለሆነ ... ወጣትነቱን የሚመኝ ማንም ሰው … በወጣትነቱ ዘመን ያመልክ የነበረውን አምልኮ … ያፈቅራት የነበረችውን (አግብቶ ያስረጃትን) ኮረዳ መልሶ ለማግኘት ቢናፍቅ አይገርምም፡፡
ሰውዬውም ወደፊት ሄደው በስውር መስመር ወደ ጥንቱ ኋላቀርነታቸው እየተመለሱ መሰለው፤ ወጣቱ፡፡ እሱ ለማጣት እየተፍጨረጨረ ያለውን እምነቱን … ሽማግሌው መልሰው ለመጨበጥ እየተፍጨረጨሩ ነው፡፡ ግን ችግር አለው፡፡ ሰውዬው የሚታወቁት በተራማጅነታቸው ነው፡፡ ኋላቀር እምነትን በመሞገት ስማቸው የገነነ … ገናና መፅሐፍት አበርክተው ብዙውን ያነቁ ናቸው፡፡
መጀመሪያ ትዝታ ወደ ኋላ … ወደ ቀድሞው እምነታቸው እንዲመለሱ እንዳበረታታቸው ሁሉ … ይሉኝታ ደግሞ ወደ ኋላ መመለሻውን ዘግቶ አጠረባቸው፡፡ ወጣቱ ድንገት ሰውዬውን እየተመለከተ፣ይሄ ሁሉ የገቡበት አጣብቂኝ ወለል ብሎ ታየው፡፡ ተገለጠለት፡፡
ነገር ግን፤ ቢገለጥለትም፤ እሱ የሚወስደው ትምህርት የለም፤ከሰውዬው ተሞክሮ፡፡ እኔም ለመተው ወደፈለኩት እምነት አንድ ቀን ማጣፊያ ሲያጥረኝ መመለሴ አይቀርም ብሎ አላሰበም። ወጣት ነው፡፡ ዞሮ መግቢያው ቢታወቀውም ከመውጣት አያግደውም፡፡ ማመፅ አለበት፡፡ ለሁሉም ጊዜ አለው፡፡
“የልደት ቀኔ የሚያስታውሰኝ … ጊዜው የእኔ መሆኑን ነው” አላቸው፤ ለአዛውንቱ፡፡ የፈለገ ቢፈትጉትም ግን የሚሰጣቸው መፍትሄ አይኖርም። ወጣቱ ሽማግሌውን ወደ መተንኮስ ድንገት አመራ። በእሳቸው ሞት የእሱ ትንሳኤ ወይንም የእሱ ዘመን እንደሚጀምር አንዳች መገለጥ ሹክ ብሎታል፡፡
“ጊዜው የእኔ መሆኑንና መፅሐፉ ለእርሶ እንደማያገለግል ነው የልደቴ ቀን የገለጠልኝ … ይኼ አባባሌ የድፍረት አይሁንብኝና … በአባባሉ ከተስማሙ ለምን መፅሐፉን እንደ ልደት ቀን ስጦታ መርቀው አያበረክቱልኝም?!”
የንግግሩ ድፍረት በሽማግሌው ውስጥ የተሸሸገ ንዴት ቀሰቀሰ … ግን ንዴታቸው በማሸት ብዛት የጠቆረ አፍንጫቸውን በኃይል ከማቅላት በላይ ሌላ መፍትሄ ሊፈጥርላቸው አልቻለም፡፡ ጋቢያቸውን በመላጣው ጭንቅላታቸውና ሽበቶቻቸው ላይ አልብሰው ወጣቱን ትክ ብለው ብቻ መመልከት ቀጠሉ፡፡ “ምናልባት በመቃብሬ ላይ ነው እንጂ በህይወት ቆሜ አንተ የእኔን መፅሐፍ አትወስድም” እንደ ማለት ፍርጥም አሉ፡፡
“በእናንተ ትውልድ ባህል መሰረት … እድሜህን ባትገልጥልኝም … መልካም ልደት ተመኝቼልሀለሁ … መፅሀፍቶቼን ግን አልሰጥህም … የማልሰጥህ ደግሞ እኔ በሄድኩበት መንገድ እንድትጓዝ ስለማልሻ ነው፡፡ ቀስ ብለህ ኑር … ቀስ ብለህ አስብ፡፡ ቀስ ብለህ አስተውል፡፡ እና ለራስህ እምነት የሚመጥን ፈጣሪ ላይ ድረስ፡፡ መድረስ ባትችል እንኳን ወደ ኋላህ ተመልሰህ “ተሳስቼ ነበር” የማያስብልህን መንገድ ያዝ፡፡ በፍጥነት ቸኩሎ መውጣት ወደ ወጣህበት በስተርጅና የሚመልስህ ከሆነ፣ መሄድ የዜሮ ድምር ዋጋ ነው የሚኖረው … በሰዓቱ መጥተህ መፅሐፉን ስለመለስክልኝ ሳላመሰግንህ አላልፍም …” አሉና ወጣቱን አሰናበቱት፡፡ ወጣቱ የተናገሩትን አልሰማም፡፡ የሚጋልብ ደሙ ጆሮውን ደፍኖታል፡፡ ዋናው ፍላጎቱ ማንበብ ነው። ማንበብና አዛውንቱ ተጉዘው የደረሱበት ላይ ደርሶ ተስፋ አለመቁረጥ። የሽማግሌውን ስህተት በትኩስ ኃይልና ተስፋ ማደስ። መታደስ እንደሚችል እርግጠኛ ነበር። ሽማግሌው ገና ባይሞቱም በወጣቱ አይን ግን እንደ አስከሬን ተቆጥረዋል፡፡ ባይሞቱም ሞተዋል። ሐውልት ሊሆኑለት እንኳን አይችሉም። ከሽማግሌው የሚፈልገው ነገር መፅሐፎቻቸውን ብቻ ነበር፡፡ ምናልባት ሲሞቱ ያወርሱኝ ይሆናል የሚል የተስፋ ጭላንጭል በውስጡ ተቀጣጥሏል። መፅሐፍቱን ሊያወርሱት እንዲችሉ የስሜት ቀብድ በሰውዬው ውስጥ ማሳደር ይኖርበታል፡፡ ሰውየው የሀሳብ እንጂ የአካል ልጅ አላፈሩም፡፡ ምናልባት የአካል ልጅነትን ተውኔት ለራሱ ፅፎ እስኪሞቱ ቢጫወት መፅሐፍቱን ጥለውልን ይሞታሉ ብሎ በማሰብ የልደት ቀኑን አሳለፈው፡፡
… ከዚህ ባሻገር የልደት ትርጉም ለእሱ የተለየ ፍቺ አልነበረውም፡፡ እድሜው 25 ---- ደሙም የስሜት የደም ግልቢያ የፈጠነ ነበር፡፡ ሰክኖ ለማሰብ የሚያስፈልገው እድሜ ስንት እንደሆነ የማወቂያ አቅም አልነበረውም፡፡    

Saturday, 25 February 2017 12:59

የፀሃፍት ጥግ

· እግዚአብሔር ልብህ ውስጥ ያስቀመጠውን ታሪክ ፃፈው፡፡
  ካሬን ኪንግስበሪ
· አንተን የተለየህ ስለሚያደርግህ ጉዳይ ፃፍ፡፡
  ሳንድራ ሲስኔሮስ
· እውነተኛ አልኬሚስቶች እርሳስን ወደ ወርቅ አይቀይሩም፤ ዓለምን ወደ ቃላት ነው የሚቀይሩት፡፡
  ዊሊያም ኤች. ጋስ
· ሕይወትህን ወደ ታሪክ ካላዞርክ፣ የሌላ ሰው የታሪክ አካል ትሆናለህ፡፡
  ቴሪ ፕራትቼት
· በውስጥህ ታሪክ ካለ፤ የግድ መውጣት አለበት፡፡
  ዊሊያም ፎክነር
· አዕምሮዬን ባዶ ለማድረግ ካልፃፍኩ አብዳለሁ
  ሌርድ ባይረን
· የማታ ማታ ሁላችንም ታሪኮች እንሆናለን፡፡
  ማርጋሬት አትውድ
· ሰው ‹‹አላነብም›› ሲል በሰማሁ ቁጥር አዝናለሁ፡፡ ምክንያቱም ‹‹አልማርም›› ወይም‹‹አልስቅም›› አሊያም ‹‹አልኖርም›› እንደ ማለት ነው፡፡
  ጄፍሬይ ዴብሪስ
· ኮሜዲ የምትፅፍ ከሆነና ሁሉንም ለማስደሰት ከሞከርክ ማንንም አታስደስትም፡፡
  ብሬንዳን ኦ’ካሮል
· እንደ ፀሃፊ ሌሎች ያልተናገሩትን ለማድመጥ ሞክር…እናም ስለ ፀጥታው ፃፍ፡፡
  ኤን. ኦር. ሃርት
· ፀሃፊ ነኝ፡፡ የምፅፈው ለገቢ ብቻ አይደለም፡፡ የምፅፈው ፀሃፊ ስለሆንኩ ነው፡፡
  ጋሪ ጄኒንግስ
· ደራሲው ካላለቀሰ፣ አንባቢው አያለቅስም፡፡
  ሮበርት ፍሮስት
· መፃፍ አስደሳች ስቃይ ነው፡፡
  ግዌንዶሊን ብሩክስ
· ደራሲነት በቋንቋ መስከርን ይጠይቃል፡፡
  ጂም ሃሪሰን

ከዕለታት አንድ ቀን በደጋማው አካባቢ የሚኖሩ ሁለት አርሶ አደሮች ነበሩ፡፡ የሚኖሩት በሳር ቤት ውስጥ ነበረ፡፡ ብዙ እርሻ ለብዙ ዓመታት አካሂደዋል፡፡ ነገር ግን ኑሯቸው ፈቀቅ አላለም፡፡ ሁሌ ከእጅ ወደ አፍ ነው፡፡
አንድ ቀን ግን አንድ የተለየ ሁኔታ በመንደሩ ታየ፡፡ ሰው ሁሉ ጉድ አለ፡፡ ይኸውም ከሁለቱ አርሶ አደሮች የአንደኛው ቤት፣የሳር ክዳኑ ተነስቶ ቆርቆሮ ለብሷል፡፡ አጥሩም እስከ ዛሬ በእሾክና በጭራሮ ታጥሮ የነበረው በአጠና ታጥሯል፡፡ የውጪ በርም በቆርቆሮ ተሰርቶለታል፡፡ አገር ጉድ ያሰኘ ነገር ተፈጠረ፡፡
የሰፈሩ ሰው መነጋገር ጀመረ፡-
1ኛው - ይሄ ገበሬ ምን ተዓምር ወርዶለት ነው እንዲህ በአንድ ጊዜ ይሄን ሁሉ ለውጥ             ያመጣው?
2ኛው - ዘርፎ መሆን አለበት እንጂ እንዲያው የሰማይ መና ቢሆንማ ለእሱ ሲዘንብ ለእኛ እንዴት አያካፋም?
3ኛው - ያን ጎረቤቱን፣ አርሶ - አደሩን ጓደኛውን ለምን አንጠይቀውም?
4ኛው - ይሄ መልካም ሀሳብ ነው፤ አለና ተያይዘው ወደ ጎረቤትየው ሄዱ፡፡ ቤቱ ቁጭ ብሎ አገኙት፡፡
“ወዳጃችን፤ አንድ ግራ ያጋባን ነገር ተፈጥሮ ነው የመጣነው!” አሉት፡፡
“ምንድን ነው? ምን ችግር ተፈጠረ?”
“ችግር አይደለም፡፡ እንዲያው የማወቅ ጉጉት ይዞን ነው፡፡ ምናልባትም እኛ ዘዴውን ካወቅነው ሊያልፍልን ይችላል፣ ብለን ነው”
“እኮ ነገሩ ምንድን ነው?” አለ እሱም የማወቅ ጉጉት ይዞት፡፡
“ይሄ ጎረቤትህና ጓደኛህ እንዲህ ባንድ ጀንበር አልፎለት፣ ቆርቆሮ ጣራ፣ የአጠና አጥር ለመስራት የቻለው፣ ምን አግኝቶ ነው? ልጆቹ ገንዘብ ላኩለት እንዳንል፣ ገና እነሱም ስደት ላይ ሆነው ለራሳቸውም በቂ ያላገኙ ናቸው፡፡ በውርስ አገኘ እንዳንል በቅርብ የሞተ ዘመድ የለውም፡፡ ሚሥጥሩ ጸነነብን፡፡ የምታውቀው ነገር ካለ ንገረን፡፡ ይሄ ዘመን አመጣሹ ሙስና የሚሉትም ከሆነ ንገረንና፣ ቁርጣችንን አውቀን ቁጭ እንበል!”
ጎረቤትየውም፤
“ወገኖቼ፤እኔም እንደናንተ ግራ ገብቶኝ ትላንትና ጠይቄው፣ ዛሬ እነግርሃለሁ ብሎ ቀጥሮኛል፡፡ ስለዚህ ማምሻውን እነግራችኋለሁ” አላቸውና ተለያዩ፡፡
የተሻሻለውን ገበሬ ያልተሻሻለው ገበሬ በቀጠሮው መሰረት አገኘው፡፡
“እህስ ወዳጄ፤ የብልፅግናህ ሚሥጥር ምንድን ነው?” አለው በቀጥታ፤ ወደ ፍሬ ጉዳዩ ገብቶ፡፡
“ምን መሰለህ ወዳጄ፤ ምንም ምስጢር የለበትም፡፡ የደጋ ወንድሞቻችን ገበሬዎች የማረሻ፣ የዶማ፣ የማጭድ፣ የአካፋ ችግር እንዳለባቸው ተገነዘብኩ፡፡ ስለዚህ በሬዎቼን ሸጥኩና ቆላ ወረድኩ፡፡ ያለ የሌለ ብረት ሰብስቤ ማረሻ በል፣ ዶማ በል፣ ማጭድ በል፣ መኮትኮቻ፣ መንሽ፣ ድጅኖ … ምኑ ቅጡ --- ቁጭ ብዬ አሰራሁ፡፡ እግረ መንገዴን ቀጥቃጩ በምን ዘዴ እንደሚቀጠቅጥ፣ በምን ዘዴ ቅርፅ እንደሚያወጣ ተማርኩ። በሁለተኛ ዙር ቆላ ወርጄ ያመጣኋቸውን ጥቂት ብረቶች እኔው ራሴ ቀጥቅጬ፣ ቀርጬ አበጀኋቸው፡፡ ከዚያ ሁሉንም ዋጋ ተምኜ፣ ገበያችን ላይ ቸበቸብኳቸው! ይሄው ነው ጉዳዩ!”
ጎረቤትየው አመስግኖት፤ “ወይ ነዶ” እያለ፣ በቀጥታ ወደ ቤቱ ሄዶ፣ በሬዎቹን ፈትቶ ገበያ አወጣቸው፡፡ ሸጧቸው ተመለሰ፡፡ በቀጣዩ ቀን ገንዘቡን ይዞ ማልዶ ቆላ ወረደ፡፡ ቆላ ያለ፣ አንድ ቁራጭ ሳይቀረው፣ ያገሩን ብረታ ብረት ሁሉ ገዛ፡፡
ብረቶቹን ተሸክሞ የደጋውን ዳገት ተያያዘው፡፡ ሆኖም ገና የደጋውን ወገብ ሳያልፍ፣የራሱ ወገብ ቅንጥስ አለና ተዝለፍልፎ ወደቀ፡፡
የሰፈር ሰዎች ወደ ቆላ ሲወርዱ ወድቆ አገኙት! በድንጋጤ፤
“ምነው አያ፤ ምን ሆነህ ነው?” ብለው ጠየቁት፡፡
“አይ ወዳጆቼ! በእኔ የደረሰ አይድረስባችሁ! ያ ወዳጄ ጎረቤቴ ገበሬ፣ የሰራኝ ሥራ፤ ሥራ እንዳይመስላችሁ። አለ እያቃሰተ፡፡
መንገደኞቹም፤ “ምን አደረገህ?” አሉት በድንጋጤ፡፡
እሱም፤ “አዬ! ትርፉን ብቻ ነግሮኝ፣ መከራውን ሳይነግረኝ!!” አላቸው፡፡
*         *       *
በአንድ ጀንበር ባለጠጋ መሆን አይቻልም፡፡ በአንድ ጀንበር ከገበሬነት ወደ ነጋዴነት መለወጥም ዘበት ነው፡፡ ከነጋዴነትም የነጋዴዎች ሁሉ የበላይ ቱጃር መሆን አይቻልም፡፡ ይሄ ተዓምር ሊፈጠር የሚችለው በሙስና ብቻ ነው! ሙስና ደግሞ ጊዜ ይውሰድ እንጂ የሚጋለጥ ነገር ነው! ዛሬ በሀገራችን በሀቅ የሚከበር፣ በሰለጠነው መንገድ የሚበለፅግ ነው የጠፋው፡፡ ይሄን መስመር ለማስያዝ እንዳይቻል፣ ትርፉን ብቻ እያሰቡ፣መከራውን ማሰብ የማይሹ መንግሥታዊ፣ ነጋዴያዊ፣ ደላላዊ አካላት እና ረብ ያለው ህጋዊ ህልውና የሌላቸው ወገኖች፤ የአሻጥር መረብ ሰርተው፣ ከራስጌ እስከ ግርጌ ዘርግተውና እግር ከወርች አስረው፤ “ለውጥ የሚባል አይታያትም!” እያሉ ይፏልላሉ፡፡ የገባውና ጨዋታው ውስጥ የሌለበት አካል ያስፈልጋል!  
የተማረ የሰው ኃይል ነገር ዛሬም አሳሳቢ ነው፡፡ በተለይ ዋና ዋና የምንላቸውን ምሁራን እያጣን ባለንበት በአሁኑ ወቅት፤ ‹‹የተተኪ ያለህ!›› የሚያሰኝ ጩኸት በየደጃፋችን እየተሰማ ነው፡፡ አሉን የምንላቸው ፕሮፌሰሮች እያለቁብን ነው! እንደ ዋዛ፣ ለዓመታት ያፈራናቸው አዕምሮአውያን፤ይቺን ዓለም እየተወ እያለፉ ነው! የቀሩንን ምሁራን ጠንቅቀን መጠበቅ አለብን፡፡
አንጋፋ ችግሮቻችንን ቀዳሚ ማድረግ ተገቢ ነው፡፡ የህግ የበላይነት የበላይ ነው! ማንም ከዚያ በላይ እንዳልሆነ እናሳይ ዘንድ ተግባራዊ ትግል እናካሂድ፡፡ በዱሮ ዘመን Bureaucratization of the party የሚል ችግር ነበር፡፡ የፓርቲ አባላት በቢሮክራሲው መዋቅር ውስጥ ተሰግስገው ቢሮክራሲውን ፓርቲ አደረጉ፤ፈላጭ ቆራጭ ሆኑ እንደ ማለት ነው፣ የግዢና የጫረታ ሥርዓት ወገናዊና ህግጋቱን የጣሰ መሆኑ ዜጎችን እጅግ ያሳዝናል፡፡ ዲሞክራሲያዊ መብቶችና ሰብዓዊ መብቶችን ከማክበር ጀምሮ በአግባቡ ተመሥርተው፣ በአግባቡ መደራጀትና መጠናከር የሚሹ ተቃዋሚ ፓርቲዎችን አቅል - እስከ ማሳጣት መድረስ አሳፋሪ ነው፡፡ ኢ-ፍትሐዊ አካሄዶች አገርን የገንዘብ ሰለባ  ወደ ማድረግ የሚንደረደሩ ናቸው፡፡
 በገዢው ፓርቲ በኩል የታየው የህዝብን ብሶት የመረዳት አዝማሚያ ደግ ነው፡፡ መፍትሄ ካልተገኘ ግን ችግር መዘመር ብቻ ነው! መልካም አስተዳደር እንደ ሰበብ ሳይሆን እንደ ትንተናዊ ምክን፣ እንደ ችግር መፍቻ፣ በትክክል ሥራ ላይ ማዋል ይገባል፡፡ የትምክህትም ሆነ የጠባብነት ድባብ ጥላውን እያጠላብን፣በሀቅ የምንቀሳቀስበት ሜዳ አለ ለማለት ያስቸግራል፡፡ በዚህ ሁሉ ውጣውረድ መካከል ዕርቅና ድርድር በገዢው ፓርቲና በተቃዋሚ መካከል ይደረጋል ስንል፤ በአዕምሮአችን የሚያቆጠቁጡ ጥያቄዎች አሉ፡፡ ‹‹የትም አይደርሱም!›› ዓይነት አመለካከት አስወግደናል ወይ?”፣ ‹‹ከእኛ ጋር እኩል ከተቀመጡ አይበቃቸውም ወይ?›› ከሚል ዕብሪት ተላቀናል ወይ? ‹‹የጊዜ ጉዳይ ነው፤ እንሠራላቸዋለን!›› ከሚል ሴራዊ አካሄድ ተገላግለናል ወይ? ‹‹ተልባ ቢንጫጫ፣ ባንድ ሙቀጫ›› ከሚል ትምክህት ነፃ ወጥተናል ወይ? እነዚህና እነዚህን የመሳሰሉ ዕሳቤዎች ካልተወገዱ፣ ‹‹የማይተማመን ባልንጀራ፣ ወንዝ ለወንዝ ይማማላል›› የሚለው ተረት፣ አሁንም አለ ማለት ነው፡፡ ይታሰብበት!!

  የትራምፕ ጉብኝት እንዲሰረዝ በ1.8 ሚ እንግሊዛውያን የቀረበው ጥያቄ ውድቅ ተደረገ

    ሃርቫርድ፣ የል እና ስታንፎርድን ጨምሮ 17 የተለያዩ የአሜሪካ ታላላቅ ዩኒቨርሲቲዎች፤ፕሬዚዳንት ዶናልድ ትራምፕ በቅርቡ ያስተላለፉትንና በፍርድ ቤት የተያዘውን የጉዞ ገደብ ትዕዛዝ በመቃወም ክስ መመስረታቸውን ዘ ኢንዲፔንደንት ዘግቧል፡፡
ትራምፕ የተለያዩ አገራት ስደተኞች ወደ አሜሪካ እንዳይገቡ ያስተላለፉት ትዕዛዝ፣ ከመላው አለም የሚመጡ የነገዋ አለማችን መሪዎችን ተቀብለን እንዳናስተምር እክል የሚፈጥር ነው፤ በጽኑ እንቃወመዋለን ሲሉ ዩኒቨርሲቲዎቹ በጋራ በመሰረቱት ክስ መግለጻቸውን ዘገባው ገልጧል፡፡ ክልከላው ሰዎች በነጻነት ወደ አሜሪካ እንዳይገቡና እንዳይወጡ በማገድ በአለማቀፍ ተማሪዎችና በቤተሰቦቻቸው ላይ ችግር ከመፍጠሩ ባለፈ፣ የአሜሪካ ዩኒቨርሲቲዎች በአለማቀፍ ደረጃ ብቁ የተማረ ሃይል ለመፍጠርና ነጻ የሃሳብ ልውውጥን እንዳያደርጉ የሚገድብ ነው ሲሉ ባለፈው ማክሰኞ በኒውዮርክ በሚገኝ የፌዴራል ፍርድ ቤት በመሰረቱት ክስ መግለጻቸውንም አስረድቷል፡፡
ባለፈው አመት ብቻ ከ1 ሚሊዮን በላይ የተለያዩ የአለማችን አገራት ተማሪዎች በአሜሪካ በሚገኙ የተለያዩ ዩኒቨርሲቲዎች ትምህርታቸውን እንደተከታተሉ የጠቆሙት ዩኒቨርሲቲዎቹ፤ 20 በመቶው ተማሪዎቹ የውጭ አገራት ዜጎች የሆኑትን የል ዩኒቨርሲቲን ጨምሮ ብዙዎቹ የአገሪቱ ዩኒቨርሲቲዎች በርካታ የውጭ አገራት ተማሪዎች፣ መምህራንና ሰራተኞች እንዳሏቸው የጠቆመው ዘገባው፤ዩኒቨርሲቲ ኦፍ ቺካጎ፣ ዩኒቨርሲቲ ኦፍ ፔንሲልቫኒያ እና ብራውን ክሱን ከመሰረቱት ሌሎች የአሜሪካ ታላላቅ ዩኒቨርሲቲዎች መካከል እንደሚገኙበትም አመልክቷል፡፡
በተያያዘ ዜናም፣ ከ1.8 ሚሊዮን በላይ እንግሊዛውያን ፊርማቸውን በማሰባሰብ የአሜሪካው ፕሬዚዳንት በቅርቡ አገሪቱን ለመጎብኘት የያዙት እቅድ እንዲሰረዝ ያቀረቡት ጥያቄ በአገሪቱ መንግስት ውድቅ መደረጉ ተዘግቧል፡፡
“የትራምፕ ጉብኝት የሁለቱን አገራት ግንኙነት የሚያጠናክር አስፈላጊ ሁነት በመሆኑ ጉብኝቱ እንዲሰረዝ የቀረበው ጥያቄ ውድቅ ተደርጓል፤ ጉብኝቱ በተያዘለት ዕቅድ መሰረት ይከናወናል” ሲል የእንግሊዝ የውጭ ጉዳይ ቢሮ ባለፈው ማክሰኞ ባስተላለፈው መልዕክት፣ በይፋ ማስታወቁን ዋሽንግተን ታይምስ  ዘግቧል፡፡
የአገሪቱ መንግስት የትራምፕን ጉብኝት በተያዘለት ዕቅድ ለማከናወን አስፈላጊውን ዝግጅት ማጠናቀቁንም ቢሮው ባወጣው መግለጫ ማስታወቁን የጠቆመው ዘገባው፤ትራምፕ በመጪዎቹ ሁለት ሳምንታት ጊዜ ውስጥ ጉብኝቱን ያደርጋሉ ተብሎ እንደሚጠበቅም ገልጧል፡፡
የእንግሊዝ ጠቅላይ ሚኒስትር ቴሬሳ ሜይ፤ ባለፈው ወር በአሜሪካ ባደረጉት ይፋዊ የስራ ጉብኝት አገሪቱን እንዲጎበኙ ባቀረቡላቸው ግብዣ መሰረት ትራምፕ ጥያቄውን መቀበላቸውን ተከትሎ፣ ከ1.8 ሚሊዮን በላይ ዜጎች ተቃውሟቸውን በመግለጽ ጉብኝቱ እንዲሰረዝ መጠየቃቸውን ያስታወሰው ዘገባው፤ የአገሪቱ ፓርላማ በመጪው ሳምንት በጉዳዩ ላይ ተከራክሮ ውሳኔ ለማሳለፍ ቀጠሮ ቢይዝም፣ ቢሮው ባወጣው መግለጫ ጥያቄው ውድቅ መደረጉን አስታውቋል፡፡

 ናይጀሪያ አሸባሪው ቡድን ቦኮ ሃራም በነዳጅ ማጣሪያዎቿ ላይ በተደጋጋሚ ባደረሳቸው ጥቃቶች ሳቢያ በ2016 ከዘርፉ ማግኘት ከሚገባት ገቢ 100 ቢሊዮን ዶላር ያህል ማጣቷን አሶሼትድ ፕሬስ ዘግቧል፡፡
    የሽብር ቡድኑ በአገሪቱ የነዳጅ ማምረቻ አካባቢዎች በሚፈጽማቸው ጥቃቶች ሳቢያ የናይጀሪያ የነዳጅ ምርት በከፍተኛ ሁኔታ መቀነሱን የነዳጅ ሚኒስትሩ ኤቢ ካቺክው ማስታወቃቸውን የጠቆመው ዘገባው፤ በየዕለቱ የምታመርተው ነዳጅ በ1 ሚሊዮን በርሜል መቀነሱን ገልጧል፡፡
አገሪቷ ባለፉት 25 አመታት የከፋውን የኢኮኖሚ ድቀት ማስተናገዷንም የጠቀሰው ዘገባው፤ የአገሪቱ መንግስት የነዳጅ ምርቱን ለማሻሻልና ኢኮኖሚው እንዲያገግም ለማስቻል እየሰራ እንደሚገኝም ጠቁሟል፡፡

 • በጥንካሬው ወደር አልተገኘለትም
                      • ከ17 አመታት በኋላ አሁንም ድረስ አገልግሎት የሚሰጡ ቀፎዎች አሉ

      ዓለማችን እጅግ በተራቀቁ ስማርት ፎኖች ከመጥለቅለቋ፣ ተች ስክሪን ሞባይል በልጅ በአዋቂው እጅ ከመግባቱ፣ ሞባይል ከመደዋወያ መሳሪያነት አልፎ እጅግ በርካታ ተግባራትን መፈጸሚያ ወሳኝ ቁስ ከመሆኑ በፊት፣ በቀዳሚነት ወደ ገበያ የገባውና እንደ ብርቅ ይታይ የነበረው፣ በጥንካሬው ዛሬም ድረስ አቻ እንደማይገኝለት የሚነገረው ኖኪያ 3310፤ እንደገና ወደ ገበያ ሊገባ መሆኑ ተዘግቧል፡፡
    የዘመናዊ የሞባይል ቀፎዎች ዘመን ጅማሬ ምልክት እንደሆነ የሚነገርለት ፈር-ቀዳጁ ኖኪያ 3310፤ በአለማችን የሞባይል ቀፎዎች ቴክኖሎጂ ታሪክ እጅግ ጠንካራውና ሃይል ቆጣቢው እንደሆነ የዘገበው ዘ ኢንዲፔንደንት፣ የሞባይል ቀፎው ከ17 አመታት በኋላ በቅርቡ እንደገና ወደገበያ ሊገባ መሆኑን ገልጧል፡፡
   የተወሰነ ማሻሻያ ይደረግበታል የተባለው አዲሱ ኖኪያ 3310፣ በዚህ ወር መጨረሻ በሚከናወነው የአለም የሞባይል ኮንግረስ ላይ ለእይታ ይበቃል ያለው ዘገባው፤ በሳምንታት ጊዜ ውስጥ በገበያ ላይ እንደሚውልና የመሸጫ ዋጋው 59 ዩሮ ይሆናል ተብሎ እንደሚጠበቅም አስረድቷል፡፡
   ኖኪያ 3310 እ.ኤ.አ በ2000 ለመጀመሪያ ጊዜ ተመርቶ ወደ ገበያ መግባቱን ያስታወሰው ዘገባው፤ ምንም እንኳን ኩባንያው ይህንን የሞባይል ቀፎ ማምረት ካቆመ 12 አመታት ቢቆጠሩም ከ16 አመታት በፊት የተመረቱና አሁንም ድረስ አገልግሎት በመስጠት ላይ የሚገኙ ቀፎዎች እንዳሉ ገልጧል፡፡ ኖኪያ ኩባንያ ከሚታወቅባቸው ስኬታማ የሞባይል ቀፎዎቹ መካከል አንዱ የሆነው ኖኪያ 3310 ለመጀመሪያ ጊዜ ለገበያ በቀረበበት ወቅት በአለም ዙሪያ 126 ሚሊዮን ያህል እንደተሸጠ የተነገረ ሲሆን፣ የተሻሻለው አዲሱ ምርት ከሳምንታት በኋላ ለአውሮፓና ለደቡብ አሜሪካ አገራት ገበያ እንደሚቀርብም ታውቋል፡፡ ኩባንያው “ኖኪያ 215”ን የመሳሰሉ የቀድሞ ተወዳጅ የሞባይል ቀፎዎቹን
እንደገና አሻሽሎ በማምረት የገበያ ድርሻውን የማስፋት ዕቅድ ይዞ እየሰራ እንደሚገኝም ዘገባው አብራርቷል፡፡

 የፊቱን ገጽታ፣ አለባበሱን፣ አነጋገሩን፣ ስሙንና አጠቃላይ ሁኔታውን ሆን ብሎ ከአዶልፍ ሂትለር ጋር
በማመሳሰል፣ በየጎዳናው ሲንቀሳቀስ የነበረው ኦስትሪያዊ፤ በፖሊስ ቁጥጥር ስር ውሎ፣ ለጨፍጫፊው ናዚ ክብር
ሰጥተሃል በሚል መከሰሱ ተዘግቧል፡፡ ሃራልድ ዜንዝ የሚለውን ወላጆቹ ያወጡለትን ስም ሃራልድ ሂትለር
ብሎ የቀየረው የ25 አመቱ ኦስትሪያዊ፤ ከጸጉር ስታይሉ አንስቶ፣ የጺም አቆራረጡንና አለባበሱን ከሂትለር ጋር
በማመሳሰል በየአደባባዩ ሲንቀሳቀስ መቆየቱን የጠቆመው ቢቢሲ፤ ጨፍጫፊውን ሂትለርን አክብረሃል በሚል
መከሰሱን ገልጧል፡፡     ግለሰቡ በመጽሃፍት መደብሮች እየተዘዋወረ የሁለተኛው የአለም ጦርነትን የተመለከቱ መጽሃፍትንና መጽሄቶችን በብዛት መግዛት ያዘወትር እንደነበር የጠቆመው ዘገባው፤ ሂትለር በተወለደበት ቤት አካባቢ በተደጋጋሚ ሲያንዣብብ መታየቱንም ጠቅሷል፡፡ ለሂትለር ክብር የሚሰጥ ድርጊት በአገሪቱ ህግ መሰረት ወንጀል መሆኑን የጠቀሰው ዘገባው፤ በብዙዎች ዘንድ “ዳግማዊ ሂትለር” ተብሎ የሚታወቀው ግለሰቡም፣ በተደጋጋሚ መሰል ድርጊቶችን ሲፈጽም መቆየቱ በምርመራ በመረጋገጡ በፖሊስ ቁጥጥር ስር ውሎ፣ ክስ እንደተመሰረተበት አመልክቷል፡፡

 የደራሲ ሚካኤል መኮንን የአጭር ልቦለድ ስብስቦችን ያካተተ “የተጣሉ ፊደላት” የተሰኘ መፅሐፍ የፊታችን ሐሙስ ከቀኑ 11፡00 ጀምሮ በዋቢ ሸበሌ ሆቴል ይመረቃል፡፡
    አጫጭር ልቦለዶቹ በህይወት ፍልስፍና፣ በአገርና በተለያዩ ማህበራዊ ጉዳዮች ላይ የሚያጠነጥኑ ናቸው ተብሏል። ሰባት አጫጭር ልቦለዶችን የያዘው መፅሐፉ፤ በ242 ገጾች ተቀንብቦ፣ በ65 ብር ከ95 ሳንቲም ለገበያ ቀርቧል፡፡መጻህፍቱን ምስጋናው መፃህፍት መደብር እንደሚያከፋፍለውም ታውቋል፡፡

የ25 ስኬታማ የሥራ ፈጣሪዎች፣የቢዝነስ መሪዎችንና ምሁራንን አጫጭር አነቃቂ ታሪኮች የያዘው “5ቱ ገፆች” የተሰኘ መፅሐፍ የፊታችን ሀሙስ ከቀኑ 11፡00 ጀምሮ በኢንተርኮንትኔንታል ሆቴል እንደሚመረቅ “ገበያ ኑ ቢዝነስ ፕሮሞሽንና ኮሚዩኒኬሽን” ገለፀ፡፡ የስኬት መፅሐፉን ፅፎ ለማጠናቀቅ ሰባት አመት እንደፈጀበት የተናገረው ሰለሞን ሹምዬ፤ መፅሀፉ ለኢንተርፕረኒሺፕ ትምህርት ማጣቀሻ ሆኖ እንደሚያገለገል ጠቁሟል።
   የመፅሐፉ መታሰቢያነት ለእናቱና ልጆቻቸውን በጥሩ ስነ-ምግባር ላሳደጉ እናቶች በሙሉ እንደሆነ የገለፀው ደራሲው፤ በዕለቱ እናቶች በሚገኙበት ‹‹እናቴ” የተሰኘና ኤልያስ መልካ ያቀናበረው ነጠላ ዜማ እንደሚለቅም ተናግሯል፡፡   ደራሲው ከዚህ ቀደም ‹‹ገመና›› የተሰኘ ረጅም ልቦለድና ‹‹ምስጢር›› የግጥም መድበል ለንባብ ማብቃቱ ይታወቃል፡፡