Administrator

Administrator

ከዕለታት አንድ ቀን አንዲት መነኩሲት ጎኅ ሲቀድ  ወደ ቤተ ክርስቲያን ሊሄዱ ይነሳሉ፡፡ አንድ ዛፍ አጠገብ ሲደርሱ ተንበረከኩና ሁለት እጃቸውን በልመና መልክ ዘርግተው፤ ጸለዩ፡፡
“አምላኬ ሆይ! ድንገት ከወትሮው ፀሎቴ አሳንሼብህ ይሆናል፡፡ የከዋክብት ብዛቱን የውቂያኖስ  ስፋቱን፣ የሙሴ በትሩን፣ የገብርኤል ተዓምሩን፣ የእመቤታችን  አማላጅነቷን የምታውቅ፣ የምትሰጥ፤ የነገሩህን የማትረሳ፣ የለመኑህን የማትነሳ፣ ሰማይን ያለ ካስማ  ያቆምክ፣ የማያርሱ  የማይዘሩ ወፎችን  የእለት ጉሮሮ የምትዘጋ፣ ምንም የማይሳንህ አምላክ  ሆይ! ካንተ ልግስና  አንፃር እጅግ  ትንሽ ነገር ነው የምለምንህ፡፡ እባክህ ዕድሜዬን ጨምርልኝ?”
ለካ ይህን ፀሎታቸውን ሲያደርሱ፣ ሁሌ ቁጥቋጦ ውስጥ ተደብቆ የሚያዳምጣቸው አንድ ተንኮለኛ የቆሎ ተማሪ ኖሯል፡፡
በሚቀጥለው ማለዳ ጎኅ በቀደደ ሰዓት ያ የቆሎ ተማሪ፣ ቀደም ብሎ ዛፍ ላይ ወጥቶ ይጠብቃቸዋል፡፡ እሳቸው እንደልማዳቸው መጥተው ፀሎትና ልመናቸውን አሰሙ፡፡ በመጨረሻም፤ “ዕድሜዬን ጨምርልኝ፣ አደራ!” አሉ፡፡
ይሄኔ፤ ያ የቆሎ ተማሪ፤
“አንቺ መነኩሲት! ምን ያህል ዕድሜ ልጨምርልሽ?” አለ ድምፁን  ጎላ አድርጎ፡፡ መነኩሲቷ ደነገጡ፡፡  ፀሎታቸው ተሰማ! ሲያስቡት ሃያም ትንሽ ነው፡፡ አርባም ትንሽ  ነው፡፡ መቶም ትንሽ ዕድሜ ነው፡፡ በመጨረሻ እንዲህ ሲሉ መለሱ፤ “አምላኬ ሆይ! አንድ ድሃን  ከነጭራሹስ እዚሁ ብትተወኝ፣ ምን እጎዳሃለሁ!” አሉ፡፡
***
የዓለም ኢኮኖሚ ጉዳይ አንጋፋ ባለሙያ የሚባለው አዳም ስሚዝ፤ “የሰው ልጅ ፍላጎት ወሰን የለውም” ያለንን ከላይ ያየነው ተረት በአበሽኛ ሳይገልጥልን አልቀረም - Human wants are unlimited ማለት ይሄው ነው፡፡ ዛሬ መጠለያ ጠየቅን፡፡ ነገ ምግብ እንጠይቃለን፡፡ ከነገ ወዲያ መንቀሳቀሻ መኪና እንፈልጋለን፡፡ ከዚያ ታዲያ  ሰፋ ያለ ግቢ እንዲኖረን እንጠይቃለን፤ ወዘተረፈ--ችግሩ የሚመጣውና የሚስፋፋው መሰረታዊ ፍላጎታችን ከተሟላ በኋላ ነው፡፡ ወለሉ ግን መሰረታዊ ፍላጎት ነው፡፡ ኢኮኖሚያችን ከዚህ ወለል  በታች ከሆነስ? “እዚሁ ላይ ነው ችግሩ” እንዳለው ነው ሼክስፒር፡፡ ”መሆን ወይስ አለመሆን?” የሚባለው ጥያቄ፣ ማናቸውም ጉዳይ ለውሳኔ አሳሳቢ ደረጃ ሲደርስ የሚመጣ ነው፡፡ ውስጥን መፈተሽ አለመፈተሽ፣ እርምጃ መውሰድ አለመውሰድ? ነው ጉዱ! ምኞት ከአቅም በላይ  መሆን እንደሌለበት ማንም ጅል አይስተውም፡፡ የፍላጎት አቅማችን እየኮሰሰ፣ ምኞታችንን ሰያጫጨው፤ የተስፋ  መቁረጥ  ጉድባ ውስጥ  እንገባለን፡፡ ዜግነታችን ራሱ ያስጠላናል፡፡ የሀገር ፍቅራችን ይሟሽሻል፡፡ ሁሉን ነገር አሉታዊ እሳቤ ውስጥ እንከተዋለን፡፡ መንገድ ተሰራ ስንባል፣ የሚሄዱበት እነሱ እንላለን፡፡ ፎቅ ተሰራ፤ “የማን ነውና!” ዘር ተጋጨ፤  ማን አመጣውና! ዕውነትም ውሸትም አለው ነገሩ፡፡ ህይወታችን የምንግዴ ህይወት ይሆናል፡፡
ሰብአዊም ሆነ ቁሳዊ ዕሴት ያለን አይመስለንም፡፡ ይሄ የተስፋ ቆራጭነት ሁኔታ (desperado state) ለሀገርም፣ ለህዝብም አደገኛ ነው! አይበጅም! የኢኮኖሚ ችግር፤ የፖለቲካ ድንግዝግዝነትን (obscurantism) ብሎም ጠርዘኝነትንና ጽንፋዊ ጥላቻን ሲፈጥር፣ “የመጣው ይምጣ” አስተሳሰብ ይከሰታል፡፡ ማህበራዊ ቀውስ፣ ሥርዓተ-አልበኝነት፣  ዘራፊነት፣ እኔ ምንተዳዬነት ወዘተ ይነግሳሉ፡፡ አጠቃላይ ድቀት ይከተላል፡፡ ማንም ስለ ማንም መጨነቁን ይተዋል፡፡ ከዚህ ይሰውረን!!
ዛሬ በሀገራችን የአሳሳች መረጃዎችና ሰነዶች መብዛት ከአቅም በላይ የደረሰ ይመስላል፡፡ የወንጀለኛ መቅጫ ህጉ አለ፡፡ የተጭበረበሩ ሰነዶች  ግን ከመፈጠር አላባሩም፡፡ ሐሰተኛ የትምህርት ማስረጃ፣ በሀሰት የተፈበረከ (Forged) ፈቃድ---ለምሳሌ፡- የህንፃ ፈቃድ፣ የቀበሌ መታወቂያ፣ የግንባታ ፈቃድ፣ የመንጃ  ፈቃድ፣ የንግድ ፈቃድ፤ አልፎ ተርፎም  የጋብቻ ሰርተፍኬት ሳይቀር  በሙስና አዋላጅነት፣  በሽበሽ ሆነዋል!  የቀረው የአመፅ ፈቃድ “በፎርጅድ” ማሰራት ብቻ ነው ተብሏል! እጅ ላይ ያለው ችግር በአግባቡ መፍትሄ ባለማግኘቱ፤ ከድጡ ወደ ማጡ መሄዳችን ግድ ሆኗል፡፡ ብዙ ነገር ካንሰር- አከል በሽታ ሆኖብናል፡፡ አሰቃቂው ነገር፤ የጉዳዩ ተዋናዮች አለቃውም ምንዝሩም፣ ህግ አውጪውም፣ አስፈጻሚውም፣ መሆናቸው ነው! እርምጃ ማን ይውሰድ? አሰኝቶናል፡፡
ህገ-መንግስቱንም፣ ህዝቡንም የረሱ አያሌ  ሹማምንት ለመኖራቸው ዛሬ ብዙ አያጣራጥርም! ህገ ወጥነት ጣራው ጋ ሲደርስ ማጣፊያው ያጥራል! “የንጉሡን ፊት አይተህ ፈገግ በል” የሚለውን ተረት፣ በየደረጃው እንደ መሪ መፈክር የያዙ በርካታ ናቸው፡፡ ሁኔታዎች ከቁጥጥር ውጪ የሆኑ ለታ ግን  ሁሉን ጥፋት በክልል ከማላከክ አልፈን የራስ ተጠያቂነት አፍጦ ይመጣል፡፡ “ባሪያ ላግዝሽ ሲሏት መጁዋን  ትደብቃለች” የሚለው ተረትም በመንግሥትና በባለሙያ መካከል ይታያል፡፡
እያደር ዕውን የሆነና የሚሆን  ግጭት፣ ፍጭት፣ ወደ ዘረኝት  አቅጣጫ ለመሄድ እርሾው የሚታይና አብሲቱ የተጣለ የሚመስልበት ሁኔታ፣ ብዙው የፖለቲካ ጨዋታ ሲሟጠጥ እንደሚሆነው ሁሉ ወደ ጡንቻ የሚሄድ፣ የደም መፋሰስ ትርዒት ማየት፣ ስለ ብዙ ሰላም ለምታወራ አገር የሚያምር ቁም ነገር አይደለም፡፡ ያለመረጋጋት አስረጅ ይሆናልና፣ ከወዲሁ መገደብና ሰላማዊ መፍትሔ መሻት አስፈላጊ ነው፡፡ ቁጣን በቁጣ መመለስ አባዜው ብዙ ነው!
የተኙት ብዙዎች፣ የተናደዱትና  የነቁት ጥቂቶች ሲሆን፣  የበሰለ አመራር በስሜታዊነት ይዋጣል፡፡ ቁጣ ቦታ የሚያገኘው  ይሄኔ ነው፡፡ መጠንቀቅ ይገባል፡፡ ሆድ ሰፊ መንግስት  an eye for an eye (ዐይን ያወጣ ዐይኑ ይውጣ)  ከሚል ጥንታዊ ህግ የተላቀቀ  ሊሆን ይገባዋል፡፡ የሠለጠነ ህግ አለውና፡፡ ህግ እንዳለ ከረሳን ግን የአልዛይመር  ምርመራ ማድረግ ነው፡፡
አሁንም የውስጥ ምርመራ ያስፈልጋል፡፡ ከአንገት በላይ ምርመራው ብቻ በቂ አይሆንምና፡፡ ትንሽ ቁስል ሰፍታ ሰፍታ የአገር ህመም የምትሆን ከሆነ፣ ጠቅላላ ምርመራ የግድ ነው፡፡ ክፍሎቻችን ሁሉ በቅጡ ይመርመሩ!!
የሚጠራቀሙ ጥቃቅን ብሶቶች፤ ልክ ጠብ ጠብ እንደሚሉ የውሃ ጠብታዎች ናቸው፡፡ ሲጠራቀሙና አቅም ሲያገኙ ጎርፍ ይሆናሉ፤ ይላሉ የጥንቱ የቻይናው ማዖ  ዜዱንግ፣ ትግላቸውን ነብሱን ይማረውና፡፡ ጫማ ልክ አልሆን ሲል እግር የመቁረጥ ፖለቲካም  አይሠራም ይላሉ፡፡ ጥቃቅንና አነስተኛ ችግሮች፣ ያለ አራሚ አንድሚያድጉ አረሞች ናው፡፡ እያደር ዙሪያ ገባውን ዳዋ እንዲውጠው  ያደርጋሉና፡፡ ከዚያ “አይጥ በበላ ዳዋ ተመታ” ነው ተከታዩ፡፡ ሀገራችን ከዚህ “ውጣ እምቢ፣ ግባ እምቢ” አጣብቂኝ የሚያወጣት መላ መምታት አለባት፡፡ ቅርቃ ውስጥ ናት፤ በሰላም  ማጣት ራስ ምታት መካከል፡፡ ቅርቃሩ ጊዜያዊ ነው ወይስ አይደለም? መመርመር ነው!!  አሁንም ጠብታዎች ጎርፍ፣ ጎርፎች ዥረቶች፣ ዥረቶች ወንዞች እንዳይሆኑ፣ ቅድመ ማስጠንቀቂያዎችን ማየት ደግ ነው፡፡ ላቲኖች፤ “ጎርፍም ያለ እርከን፣ ምራቅም ያለ ከንፈር አይቆምም፡፡” ያሉትን ልብ ማለት ይጠቅመናል፡፡

•    ኮንሶዎች በኮሪደር ልማቱ አሻራቸውን እያስቀመጡ ነው


የተፈጥሮ ሃብት ልማትን ለመጠበቅ ፈታኝ የሆነውን መልከዓ ምድር በእርከን ስራ  ለእርሻ  ያዋሉትና ተፈጥሮን  ተንከባክበው በትውልድ ቅብብሎሽ  ያቆዩት የድንቅ ባህል ባለፀጋዎች ናቸው፤ የኮንሶ ማህበረሰቦች፡፡
ህይወታቸው በእጅጉ ከተፈጥሮ ጋር የተቆራኘው የኮንሶ ማህበረሰቦች፤ ተፈጥሮን በመጠበቅና በመንከባከብ ይታወቃሉ፡፡ ኮንሶዎች ከተፈጥሮ ጋር ባደረጉት የረጅም አመታት ትግል የአካባቢውን መልክዓ-ምድር በባህላዊ የእርከን ሥራ በፈለጉት መንገድ ለመቀየርና ለመጠቀም የቻሉ ሲሆን፤ በዚህም ከሀገራቸው አልፈው ዓለምን በማስደመም የራሳቸውን  ታሪክ ሠርተዋል።
ኤ.አ.አ. በ2011 ዓ.ም በዩኔስኮ በዓለም ቅርስነት የተመዘገበው የኮንሶ ማራኪ መልክዓ-ምድር፤ 23 ሺህ ሄክታር መሬት ላይ ያረፈ ነው፡፡ መልክዓ- ምድሩ፣ በውስጡ በተለያዩ ባህላዊ ዘዴዎች  የተሰሩ እርከኖችና ካቦች የታጠሩ መንደሮች እንዲሁም ጥብቅ ደኖችን ጭምር ያካተተ ነው፡፡ የኮንሶ የድንጋይ እርከኖች በዓይነታቸውም ሆነ በአሰራራቸው ውበትን የሚያጎናፅፉና የአካባቢውን መልከዓ-ምድር የሚጠብቁ ናቸው፡፡
ለኮንሶዎች ብቻ ሳይሆን እንደ ሀገር ኩራት የሆነው ባህላዊ የእርከን አሰራር በኮንሶ ብቻ  ሳይገደብ፣ 24 ሰዓት ሳታንቀላፋ ለእድገት በምትታትረው የአፍሪካ መዲና አዲስ አበባም እየተተገበረም  ይገኛል፡፡ ኮንሶዎች  የከተማ አስተዳደሩ ትኩረት ባደረገባቸው  የእንጦጦና  ሌሎች የኮሪደርና የወንዝ ዳርቻ ልማት ፕሮጀክቶች ላይ የእርከን ሥራ ጥበባቸውን መተግበር  ከጀመሩ ሰነባብተዋል፡፡ በዚህ ሥራቸውም  በመዲናዋ  ላይ  አሻራቸውን እያሳረፉ  ይገኛሉ።
በኮሪደር ልማቱ የአፈር መሸርሸር እንዳይከሰት የእርከን ስራዎችን ሲያከናውኑ ያገኘናቸው ከኮንሶ ማህበረሰብ የመጡት የእርከን ሥራ  ባለሙያ አቶ አማኑዔል አክመል፣ተወልደው ያደጉት በደቡብ ኢትዮጵያ ኮንሶ ዞን ከአራት ከተማ ሲሆን፤ በደንና መሬት ጥበቃ ሥራ ላይ መሰማራታቸውን   ይናገራሉ፡፡
“እኔ ከመጣሁ ጀምሮ እስከ አሁን እየሰራን ያለነው በወንዞች ዳርቻ ሲሆን፤  የኮሪደር ልማት ስራዎቹ በጣም በጥሩ ሁኔታ እየተካሄዱ  መሆናቸውን አይተናል። የኮንሶ ልጆችም እርከኑን በመስራት አሻራቸውን እያስቀመጡ ናቸው፡፡ በእኔ በኩልም ቱሪስቶች ሊጎበኙት የሚችል፣ውብና ጥራት ያለው  ስራ ሰርተን ከተማችን ላይ አሻራችንን ማስቀመጥ እንፈልጋለን፡፡ አሁንም ከመንግሥት ጋር በኮሪደር ልማት ዙሪያ ጠንካራ ሥራዎችን  እየሰራን እንገኛለን፡፡” ብለዋል፤ አቶ አማኑዔል፡፡
በኮሪደር ልማቱ ስለተፈጠረላቸው የሥራ እድልም ሲናገሩ፤ “ለበርካታ ኮንሶ ወጣቶች የስራ እድል ከመፈጠሩ ባሻገር ከምናገኘው ገቢ በመቆጠብ ቤተሰቦቻችንን ለመርዳት እንዲሁም ወደፊት ለመነገድም ሆነ በተለያየ ሙያ ለመሰማራትና ኑሮአችንን ለማሻሻል የምንችልበት አጋጣሚ ተፈጥሮልናል፡፡” ይላሉ፡፡


የኮንሶ የእርከን አሰራር ከቅድመ አያቶቻችን  ሲወርድ ሲወራረድ የመጣ ነው የሚሉት አቶ አማኑዔል፤ ይህ ጥንታዊ የሆነ  የእርከን ሥራ ኮንሶን በዩኔስኮ እንድትመዘገብ ያደረገ ጥበብ  መሆኑን  ያወሳሉ፡፡ እኛም አባቶቻችን ያስረከቡንን ጥበብ  ይዘን በዚህ የልማት ስራ ለከተማዋ ብቻ ሳይሆን ለልጆቻችንም ጭምር አሻራችንን እያኖርን ነው፤ብለዋል፡፡
“በተለያየ ምክንያት ወደ መዲናዋ የሚመጡ የኮንሶ ልጆች በእኛ እጅ የተሰሩ ስራዎችን ሲያዩ፣ እነሱም የራሳቸውን  ታሪክና አሻራ ለማኖር መነቃቃት  ይፈጥርላቸዋል።” ሲሉም አክለዋል፡፡
የእርከን ስራዎች ዋና ዓላማ መሬት በጎርፍ እንዳይሸረሸር መከላከልና አካባቢን ማስዋብ  መሆኑን የገለጹት አቶ አማኑኤል፤ እኛም በአካባቢያችን ለእርሻ አስቸጋሪ የሆኑ ቦታዎችን በማስተካከልና እርከን በመስራት ነው የምንጠቀመው፤ ብለዋል፡፡ ከልምድና ተሞክሮአችን ተነስተን ከኮንሶ በተሻለ ሥራውን በማስፋትና በማጠናከር እንሰራለን ሲሉም ተናግረዋል፡፡


የእርከን ሥራ በህብረትና በአንድነት መሥራትን ይፈልጋል ይላሉ፤ አቶ አማኑኤል፡፡ ምክንያቱንም ሲያስረዱ፤ “የእርከን ሥራ  የተለያዩ አሰራሮችን በየደረጃው የሚፈልግ ነው፡፡ አንዱ መሰረት ሲጥል ሌላው ድንጋይ ይጠርባል፤ የተጠረበውን ድንጋይ ሌላው ሲደረድር  አፈር የሚሞላም አለ፤ ስራው የሰው ኃይል ስለሚፈልግ እነዚህን ተግባራት  በሙሉ አቅም ለመፈፀም በህብረት መስራት ያስፈልጋል፡፡” ብለዋል፡፡
“በህብረት በመስራታችን ደግሞ ህብረ-ብሄራዊነትን፣ አንድነትንና ኢትዮጵያዊነትን እያሳየን ነው፡፡ ይህ ለወደፊቱ የብልፅግና ጉዞ መሰረት ነው ብዬ አስባለሁ፡፡” ሲሉ አስተያየታቸውን ሰጥተዋል፡፡
ሌላው የእርከን ሥራ  ባለሙያ ደግሞ አቶ ያቤና ያኬሳ ይባላሉ፡፡ ከደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ከኮንሶ ዞን ከነአ ወረዳ ነው የመጡት፡፡ እዚህ አዲስ አበባ የመጡት ከአዲስ አበባ ከንቲባ ፅ/ቤት በተደረገላቸው ጥሪ፣ በከተማዋ የወንዝ ዳርቻ ልማት ላይ ለመሳተፍ መሆኑን   ይናገራሉ፡፡
በከተማዋ እየተከናወነ ያለውን የወንዝ ዳርቻ ልማት በተመለከተ በሰጡት አስተያየት፤ “እጅግ በጣም የሚያኮራ የልማት ሥራ እየተሰራ እንደሚገኝ ለማየት ችለናል፡፡ እኛም በልማቱ  እየተሳተፍን በመሆናችን  በጣም ደስተኞች ነን፡፡” ብለዋል፡፡
በአዲስ አበባ የተፈጠረላቸውን የሥራ እድል አስመልክቶ ሲናገሩም፤ ለኮንሶ ልጆች ትልቅ የሥራ ዕድል መፈጠሩን ጠቁመው፣ እዚህ  በቀን የሚያገኙት ዕለታዊ ገቢ በኮንሶ ከሚያገኙት ጋር  ጨርሶ የሚነጻጸር እንዳልሆነ ይናገራሉ፡፡    
“እኛ ጥቅምት ላይ በመጀመሪያ ዙር የመጣን ነን፤ስድስተኛ  ወራችንን ይዘናል፡፡ በኮንሶ እለታዊ ገቢያችን ዝቅተኛ ነበር፡፡ እዚህ ምግብና ልብስን ሳይጨምር በቀን 650 ብር እናገኛለን፤ በወር ከ19 ሺ ብር በላይ ይደርሰናል፡፡ ይህ ደግሞ ለአንድ አርሶ አደር ቀላል የሚባል አይደለም፡፡” ብለዋል፡፡
በዚህ ገቢም የቤተሰቦቻቸውን ኑሮ እየቀየሩበት፣ ልጆቻቸውን እያስተማሩበትና የተቸገሩ ዘመዶቻቸውን እየረዱበት መሆኑን  ያስረዳሉ፡፡ ሥራው በጣም አድካሚ ቢሆንም፣ የዚያኑ ያህል ተጠቃሚ መሆናቸውን አልሸሸጉም፡፡
  መጀመሪያ ላይ በዚህ ሥራ ላይ  ከኮንሶ የመጡ 50 ባለሙያዎች ብቻ ተሰማርተው   እንደነበር ያስታወሱት አቶ ያቤና፤ አሁን ላይ ከ400 ያላነሱ ባለሙያዎች እየተሳተፉ እንደሚገኙ ተናግረዋል፡፡  
የኮንሶ ባህላዊ የእርከን ሥራ ታሪካዊ ዳራን በተመለከተ ሲያብራሩም፤ “የኮንሶ ማህበረሰብ በተፈጥሮው ታታሪ ህዝብ ነው፡፡ መልክዓ ምድሩም ሲታይ አብዛኛው ተራራማ፣ አሸዋማና ዝናብ አጠር   ነው፡፡
ይሄ  አካባቢ ታዲያ በምን አይነት ዘዴ ነው ለረጅም አመታት የኖረው ቢባል በአፈርና ውሃ ጥበቃ ዘዴ ነው፡፡ ይህም ከጥንት ጀምሮ አፈር በጎርፍ ተጠርጎ እንዳይሄድ ሲሰራበት የኖረና እንደ ባህል የተወሰደ ልምድ በመሆኑ ከትውልድ ትውልድ እየተሸጋገረ እኛ ዘንድ ደርሷል፡፡ እኛም እዚህ ተገኝተን ልምዳችንንና አሻራችንን እያኖርን ነው፡፡” ብለዋል፡፡


  ከደቡብ ኢትዮጵያ ኮንሶ ዞን  የመጡት አቶ ከድረው ገበየሁ እንዲሁ በመዲናዋ እየተከናወነ በሚገኘው የወንዝ ዳርቻ ልማት ላይ የተለያዩ የእርከን ካብ ስራዎችን እየሰሩ እንደሚገኙ ይናገራሉ፡፡ ከእንጦጦ ተራራ ወደ ከተማው የሚፈሰው ወንዝ አፈሩን እንዳይሸረሽር፣ የጎርፍ መጥለቅለቅ እንዳይከሰትና የተክሎቹ ስር እንዳይነቃቀል እንዲሁም የወንዝ ዳርቻዎችን ውበት ለማስጠበቅ የእርከን ስራ እየተሰራ መሆኑን ያስረዳሉ፡፡
ሥራውን የለመድነው ከአያቶቻችን በማየት ነው የሚሉት አቶ ከድረው፤ የአዲስ አበባ  ወጣቶችም  ከእኛ ልምድ ቢቀስሙና ከተማቸውን ቢያለሙ ተጠቃሚ ይሆናሉ ባይ ናቸው፡፡
“እኛ በአሁኑ ወቅት እየሰራን በምናገኘው ገንዘብ ህይወታችንን እየቀየርን ነው፤በዚህም በጣም ደስተኞች ነን፤ሥራችን አልቆ ጥርት ያለ ውሃ በወንዝ ሲፈስ ስናይ ደግሞ ከዚህ የበለጠ ደስተኞች እንሆናለን፡፡” ሲሉም ስሜታቸውን  ገልጸዋል፡፡
ከኮንሶ ምድር መጥተው በኮሪደር ልማቱ ላይ እየተሳተፉ ያሉና ያነጋገርናቸው ባለሙያዎች በሙሉ  ይህንን መልካም የሥራ ዕድል ለፈጠሩላቸው የአዲስ አበባ ከንቲባ አዳነች አቤቤና ጠ/ሚኒስትር ዶ/ር ዐቢይ አህመድ ልባዊ ምስጋናቸውን አቅርበዋል፡፡ በዚህ አጋጣሚ ይሄ ከኮንሶ ምድር አልፎ በመዲናዋ የኮሪደር ልማት ላይ እየተተገበረ የሚገኝ የኮንሶ ባህላዊ የእርከን ሥራ በክልሎችም ቢዳረስ ጠቀሜታው የትየለሌ ነው ብለን እናምናለን፡፡

የኢትዮጵያ ብሔራዊ ባንክ የገንዘብ ፖሊሲ ኮሚቴ፣ የዋጋ ግሽበቱን ወደ ነጠላ አሃዝ ለማውረድ ጥብቅ የገንዘብ ፖሊሲ ማስቀጠል እንደሚገባ አመልክቷል። ኮሚቴው ከቅርብ ጊዜ ወዲህ የሚታየው የውጭ ምንዛሪ አስተዳደር ጉዳይ ልዩ ትኩረት እንደሚያስፈልገው አሳስቧል።
የገንዘብ ፖሊሲ ኮሚቴ ባለፈው ማክሰኞ መጋቢት 16 ቀን 2017 ዓ.ም፣ ሁለተኛ ስብሰባውን ያካሄደ ሲሆን፤ በገንዘብ ፖሊሲው ተግባራዊ የሚደረጉ የፖሊሲ ምክረ ሃሳቦችን በዝርዝር አቅርቧል። ኮሚቴው የዋጋ ግሽበትን፣ የፊስካል ፖሊሲ ትግበራን፣ የውጭ ኢኮኖሚን፣ የገንዘብ አቅርቦትና የፋይናንስ ዘርፍ እንቅስቃሴዎችን፣ እንዲሁም  በአገር ውስጥ የማክሮ ኢኮኖሚ ሁኔታዎች ላይ ከፍተኛ አንድምታ ያላቸው ዓለም አቀፍ ሁኔታዎችን በግምገማ ቃኝቷል።
ካለፈው የገንዘብ ፖሊሲ ኮሚቴ ስብሰባ ወዲህ፣ ዓመታዊ የዋጋ ግሽበት እየቀነሰ በመምጣት በየካቲት ወር 2017 መጨረሻ፣ 15.0 በመቶ መድረሱን ኮሚቴው ገልጿል፡፡ ባለፉት ጥቂት ወራት የዋጋ ግሽበት በተከታታይ እየረገበ የመጣው፣ ብሔራዊ ባንክ ጥብቅ የገንዘብ ፖሊሲ በመከተሉ፣ የግብርና ምርት በመሻሻሉና በአስተዳደራዊ ዋጋዎች ላይ እየተወሰደ ያለው ማሻሻያ ቀስ በቀስ በመተግበሩ ምክንያት እንደሆነ ኮሚቴው አመልክቷል፡፡
 ምግብ-ነክ የዋጋ ግሽበት በየካቲት ወር 2017 መጨረሻ 14.6 በመቶ የደረሰ ሲሆን፤ ይህም ዓምና በተመሳሳይ ወቅት ከነበረው 3 በመቶ ጋር ሲነጻጸር በእጅጉ ያነሰ ነው ተብሏል፡፡ በተመሳሳይ፣ ምግብ-ነክ ያልሆነ የዋጋ ግሽበት ካለፈው ዓመት ቀንሶ 15.6 በመቶ የደረሰ ቢሆንም፣ ባለፉት ጥቂት ወራት የማንሰራራት አዝማሚያ ማሳየቱ ተጠቁሟል፡፡
በአብዛኛዎቹ የአገሪቱ አካባቢዎች የታየው ምቹ የመኸር ዝናብ ወራትና በግብርናው ዘርፍ እየተወሰዱ ያሉ የአቅርቦት ማሻሻያ ውጥኖች በዘንድሮው ዓመት ከፍተኛ የሰብል ምርት እንደሚኖር ማሳያ መሆናቸውን ኮሚቴው አንስቷል፡፡ በሌሎች ዘርፎችም፣ በተለይም በኢንዱስትሪ፣ በሸቀጦች ወጪ ንግድ (በተለይም በቡናና በወርቅ)፣ እንዲሁም በአገልግሎት ወጪ ንግድ (በተለይም በአየር ትራንስፖርትና በቱሪዝም) ዘርፎች የተጠናከረ ዕድገት እንደሚኖር ኮሚቴው ግምቱን አስፍሯል፡፡
ካለፈው የገንዘብ ፖሊሲ ኮሚቴ ስብሰባ ወዲህ የገንዘብ ዝውውር እድገት መጠነኛ ጭማሪ ያሳየ ሲሆን፤ ይህም ሊሆን የቻለው የብድር፣ የፊስካልና የውጭ ኢኮኖሚ ሁኔታዎች ላላ በመደረጋቸው ነው ተብሏል። እስከ ጥር ወር 2017 ድረስ በኢኮኖሚው  ውስጥ የሚዘዋወረው የጠቅላላ ገንዘብ አቅርቦት (broad money supply) የ22.8 በመቶ፣ መሰረታዊ ገንዘብ (base money) 42.0 በመቶ ዓመታዊ ዕድገት ሲያሳዩ፤ የሀገር ውስጥ ብድር በ19.8 በመቶ መጨመሩ ተመላክቷል፡፡ መሰረታዊ ገንዘብ ፈጣን ዕድገት ሊያሳይ የቻለው የኢትዮጵያ ብሔራዊ ባንክ ከወርቅ ሽያጭ ጋር በተያያዘ ከፍተኛ የውጭ ምንዛሪ ክምችት በመያዙና ተመጣጣኝ የአገር ውስጥ ገንዘብ ወደ ባንክ ስርዓት እንዲገባ በመደረጉ ነው፡፡
የገንዘብ ፖሊሲ ኮሚቴ እስካሁን የታየው የዋጋ ግሽበትን የመቀነስ ጥረት አበረታች መሆኑን በመጥቀስ፣ የዋጋ ግሽበት አሁንም ቢሆን ከተጠበቀው በላይና በመካከለኛው ጊዜ ከሚደረስበት ከነጠላ አሃዝ ግብ ከፍ ያለ እንደሆነ አስታውቋል። በመሆኑም የዋጋ ግሽበት ትርጉም ባለው መልኩ እስኪቀንስ ድረስ አሁን ያለው ጥብቅ የገንዘብ ፖሊሲ አቋም ተገቢ በመሆኑ ሊቀጥል እንደሚገባ መስማማቱ ተገልጿል፡፡
በተጨማሪም  ከቅርብ ጊዜ ወዲህ የሚታየው የውጭ ምንዛሪ አስተዳደር ጉዳይ ልዩ ትኩረት ሊሰጠውና ወደ ኢኮኖሚው የሚገባው የገንዘብ መጠን በገንዘብ ፖሊሲው ላይ ያልተፈለገ አሉታዊ ተጽዕኖ እንዳያሳድር መጠንቀቅ እንደሚያሻ ኮሚቴው አሳስቧል፡፡
የገንዘብ ፖሊሲ ኮሚቴ ከፍ ብሎ “ይታያል“ ያለውን የዋጋ ግሽበት ለመቀነስና በውጭ ምንዛሪ ተመን ረገድ የሚታዩ ግምታዊ አስተሳሰቦችን (expectations) ለመቆጣጠር ሲባል የብሔራዊ ባንክ የፖሊሲ ተመን (National Bank Rate) አሁን ባለበት 15 በመቶ እንዲቆይና በወለድ ተመን ላይ ወደ ተመሰረተ የገንዘብ ፖሊሲ አስተዳደር ስርዓት የሚደረገው ሽግግር ገና በመሆኑ በባንኮች የብድር ዕድገት ላይ የተቀመጠው 18 በመቶ ገደብ እንዲቀጥል መወሰኑን  ባወጣው መግለጫ አመልክቷል።

ባልደራስ ለዕውነተኛ ዴሞክራሲ ፓርቲ፣ ሰሞኑን  ለሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የቀረበውንና የመንግሥት ሠራተኞች ከሚከፈላቸው የተጣራ የወር ደሞዝ ላይ ክፍያ እንዲፈጽሙ የሚያስገድደውን  የአደጋ ስጋት ፈንድ ረቂቅ አዋጅ እንደሚቃወም ገለጸ፡፡ ፓርቲው  የመንግሥት ሰራተኞች ለመንግሥት ታጣቂ ሃይሎች የገንዘብ መዋጮ እንዲያዋጡ እየተገደዱ ነው ሲል ነቅፏል፡፡  
ባልደራስ ለዕውነተኛ ዴሞክራሲ ፓርቲ ከትላንት በስቲያ  ሐሙስ መጋቢት 18 ቀን 2017 ዓ.ም. ባወጣው መግለጫ፤ በረቂቅ ዓዋጅነት ለሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የቀረበውን የአደጋ ስጋት ክፍያን የተቃወመ ሲሆን፣ የቀረበው ረቂቅ ዓዋጅ የመንግሥትና የግል ድርጅት ተቀጣሪ ሰራተኞች ከሚከፈላቸው የተጣራ የወር ደመወዝ ላይ ክፍያ እንዲፈጽሙ የሚያስገድድ ድንጋጌ  ማካተቱ፣ “በኑሮ ውድነት የሚፈተነውን ሕዝብ ለሌላ ዙር ችግር የሚጋብዝ ነው፡፡” ሲል ተችቶታል፡፡ ፓርቲው አክሎም፤ “በሥርዓት ሰራሽ ጦርነትና የኑሮ ውድነት እየተፈተነ የሚገኘው የኢትዮጵያ ሕዝብ፣ ተጨማሪ ዕዳ ውስጥ እንዲገባ ማድረግ ሥርዓታዊ ክፋትን ያረጋግጣል” ብሏል፡፡
“አሁን ያለው የሰራተኛ አጠቃላይ ወጪና ገቢ ሲታይ፣ አገዛዙ የዚህ አገር ዜጎች በአገራቸው ነፍሳቸውን ለማቆየት በሚያስችል ደረጃም ቢሆን በልተው እንዳይኖሩ እየፈለገ መሆኑን የሚያሳይ ተግባር ተደርጎ ሊወሰድ ይችላል” ያለው ፓርቲው፤ በዓለም አቀፍ ደረጃ የዋጋ ንረትን የሚከታተሉ የተለያዩ የምርምር ተቋሞች በአሁኑ ጊዜ በኢትዮጵያ ያለው የዋጋ ንረት ደረጃ ከ60 በመቶ እንዳለፈ መጠቆማቸውን አመልክቷል፡፡ “የኑሮ ውድነቱ በዚህ እጅግ አስከፊ ሁኔታ ላይ እያለ፣ ሠራተኛው ከወር ወር አላደርስ ያለውን ገቢ በሃይል በመቀነስ፣ በየክልሉ የሚያካሂደውን ጦርነት ለመደጎም እየተጠቀመበት ይገኛል” ሲልም ባልደራስ መንግሥትን ወንጅሏል፡፡
የአደጋ ስጋት ምላሽ ፈንድ  ረቂቅ ዓዋጅ፣ የመንግስትና የግል ሰራተኞች ከሚከፈላቸው የተጣራ የወር ደመወዝ ላይ ክፍያ እንዲፈጽሙ ግዴታ የሚጥል ሲሆን፤ ባንኮች፣ አነስተኛና ጥቃቅን የፋይናንስ ድርጅቶች ከሚሰጡት የብድር መጠን ላይ፣ እንዲሁም ሌሎች የፋይናንስ ተቋማት ተጠቃሚዎች ከሚከፍሉት  የአገልግሎት ክፍያ እንደሚሰበሰብ ይደነግጋል፡፡
በሌላ በኩል፣ የመንግሥት ሰራተኞች ለመንግሥት ታጣቂዎች የገንዘብ መዋጮ እንዲያዋጡ እንደሚገደዱ የጠቆመው ፓርቲው፤ በአማራ ክልል፣ ሰሜን ሸዋ ዞን የመንግሥት ሠራተኞች ለመንግሥት ታጣቂዎች ዕርዳታ ከደመወዛቸው ሰባት በመቶውን በግዴታ እንዲያዋጡ መፈረማቸውን አመልክቷል፡፡
 “አገዛዙ እየፈፀመ ያለውን አውዳሚ ጦርነትና በሕዝብ ላይ እየተገበረ ያለውን አግባብ ያልሆነ ምዝበራ እንዲያቆም እንጠይቃለን” ያለው ባልደራስ ለዕውነተኛ ዴሞክራሲ ፓርቲ፤ የኢትዮጵያ ሕዝብ ለዘላቂ ደህንነቱ መከበር ሰላማዊ ትግልን በመከተል “እንዲታገል ጥሪ እናቀርባለን” ብሏል፣ በመግለጫው።

በተለያዩ የአገሪቱ ክፍሎች የሚንቀሳቀሱ ዜጎች ታግተው፣ አጋቾቻቸው በሚሊዮን የሚቆጠር ገንዘብ ለማስለቀቂያ እየጠየቁባቸው እንደሚገኙ የተናገሩት የመላው ኢትዮጵያ አንድነት ድርጅት (መኢአድ) ሊቀ መንበር  አቶ አብርሃም ጌጡ፤ መንግስት መንግስታዊ ሚናውን ተወጥቶ፣ ዕገታ የሚፈጽሙ ዜጎችን ወደ ሕግ ተጠያቂነት ማምጣት ግዴታው እንደሆነ ገልጸዋል። “ሰላም በምኞት አይመጣም፤ በጸሎትም አይመጣም። ሰላም በትግል ነው የሚመጣው” ብለዋል፤ አቶ አብርሃም።
የመኢአድ ሊቀመንበር  ከአዲስ አድማስ ጋር ባደረጉት ቆይታ፣ ላለፉት ስድስት ዓመታት ዜጎች በሰቆቃ እንዲኖሩ መገደዳቸውን ጠቁመው፤ “ግድያዎች፣ መፈናቀሎች፣ ዕገታዎችና የእርስ በርስ ጦርነቶች የተለመዱ ሆነዋል፤ ብለዋል - በተለይም  የአማራ ብሔር በማንነቱ ተለይቶ ጥቃት እየደረሰበት መሆኑን በመግለጽ፡፡
መኢአድ ከዓመታት በፊት፣ ከዩኒቨርስቲ የታገቱ ወጣት ተማሪዎችን በተመለከተ፣ ጠንከር ያለ መግለጫ ማውጣቱን ጠቅሰው፣ “በተለያዩ የአገሪቱ አካባቢዎች፣ ያልተነገሩ ሌሎች መከራና ስቃዮች አሉ” ሲሉ  አስረድተዋል፣ አቶ አብርሃም።
አክለውም፣ የመንግስት ቀዳሚ ሃላፊነቱ ከስሩ ባለው የጸጥታና የአመራር መዋቅር አማካኝነት የዜጎችን ሰላምና ደህንነት ማስጠበቅ መሆኑን ገልጸዋል።
“መንግስት መንግስታዊ ሃላፊነቱ ቀለም መቀባት አይደለም። ችግኝ መትከል አይደለም። የመንግስት የመጀመሪያ ሃላፊነቱ ሕግና ስርዓትን ማስጠበቅ ነው” የሚሉት አቶ አብርሃም፤ “ይሁንና መንግስት ይህንን ሃላፊነቱን እየተወጣ አይደለም።” ብለዋል።
 “ከአዲስ አበባ ወደ ጅማ፣ ወይም ከአዲስ አበባ ወደ ሐዋሳ፣ አሊያም ከአዲስ አበባ ወደ ሌላ ቦታ በሚደረጉ ጉዞዎች ላይ ዕገታዎች እንደሚፈጸሙ አልሰማንም።
 ወደ ደብረብርሃን በሚደረጉ የአውቶቡስ ጉዞዎች ላይ ዕገታዎች እንደተፈጸሙ የሚያስረዱ መረጃዎችንም በአብዛኛው አልሰማንም። ከደጀን ወደ አዲስ አበባ በሚመጡ አውቶብሶች ላይ -- ያውም አሊዶሮ በተባለ አካባቢ ላይ - በተደጋጋሚ የዕገታ ድርጊት የሚፈጸመው ለምንድን ነው?” ሲሉ አቶ አብርሃም ጠይቀዋል። “መንግስት እንደ መንግስት ተጠያቂነት አለበት። በዜጎች ላይ ለሚፈጸሙ የሰብዓዊ መብት ጥሰት በቅድሚያ የሚጠየቀው መንግስት ነው። ምክንያቱም በአሁኑ ወቅት በስልጣን ላይ የሚገኝ በመሆኑ  ነው።” ብለዋል፡፡

 •ከ12 እስከ 15 ሺ የሚደርስ  ሕዝብ ይሳተፋል ተብሏል
                              ከሦስት ወራት በኋላ የድርጅቱ ሆስፒታል ይመረቃል


       ከተመሰረተ 31 ዓመታትን ያስቆጠረው ሜሪጆይ ኢትዮጵያ የበጎ አድራጎትና የልማት ድርጅት፣ ከብራይት  አድቨርትና ኢቨንት ጋር በመተባበር፣ የገቢ ማሰባሰቢያ ሩጫ መርሐ ግብር ሊያካሂድ መሆኑን ገልጿል።
ባለፈው ረቡዕ መጋቢት 10 ቀን 2017 ዓ.ም፣ በዮድ አቢሲንያ የባሕል ምግብ አዳራሽ ለመገናኛ ብዙሃን ባለሙያዎች በተሰጠው ጋዜጣዊ መግለጫ፣ የገቢ ማሰባሰቢያ ሩጫው መጋቢት 28 ቀን 2017 ዓ.ም. ጠዋት በዑራኤል አድርጎ ወደ ወሎ ሰፈር በሚወስደው የፒኮክ መናፈሻ አዲሱ አስፋልት መንገድ በመዝለቅ፣ የወሎ ሰፈርን አደባባይ ዞሮ በታችኛው አስፋልት ወደ መነሻው በመመለስ የሚጠናቀቅ መሆኑ ተጠቁሟል፡፡  ሩጫው የሚሸፍነው አጠቃላይ ርቀት 5 ኪሎሜትር ሲሆን፣ በዚህ መርሐ ግብር ላይ ከ12 እስከ 15 ሺ የሚደርስ  ሕዝብ ይሳተፋል  ተብሎ እንደሚጠበቅ ተነግሯል፡፡
ለመርሐ ግብሩ ተሳታፊዎች የአዋቂና ሕጻናት ቲ-ሸርት መዘጋጀቱ የተገለጸ ሲሆን፤ ቲ-ሸርቶቹ ለአዋቂ 500 ብር፣ ለሕጻናት 300 ብር እንደሚሸጡ  ታውቋል፡፡  ቲ-ሸርቶቹን በሁሉም የሜሪጆይ ኢትዮጵያ ቢሮዎች  (በአስኮ ፣ በመገናኛ፣ በጊዮርጊስና ገዳም ሰፈር) እንዲሁም በዋና ዋና የዳሽን ባንክ ቅርንጫፎች (በልደታ፣ በጣና ገበያ ፣ በአድዋ አደባባይ፣ በፒያሳ፣ በጦር ሐይሎች፣ በቄራ፣ በንፋስ ስልክ፣ በቦሌ መድሃኒያለምና በሰሚት ቅርንጫፎች) ማግኘት እንደሚቻል ነው የተገለጸው።
የሜሪጆይ ኢትዮጵያ መስራችና ዋና ስራ አስፈጻሚ ሲስተር ዘቢደር ዘውዴ ባስተላለፉት መልዕክት፤ “አረጋውያንን እመግባለሁ፣ ጤንነቴን እጠብቃለሁ” በሚል መሪ ቃል በሚካሄደው የገቢ ማሰባሰቢያ ሩጫ መርሐ ግብር ላይ፣ ሁሉም ለበጎ አድራጎት ስራ ተነሳሽነት ያለው ዜጋ እንዲሳተፍ ጥሪ አቅርበዋል።
 መቶ ሕጻናትን በመርዳት ሥራውን ሀ ብሎ የጀመረው ሜሪጆይ ኢትዮጵያ፤ በአሁኑ ወቅት ከአንድ ነጥብ አምስት ሚሊዮን በላይ ወገኖችን እየረዳ እንደሚገኝ ሲስተር ዘቢደር ገልጸዋል። በተጨማሪም፣ “ኢትዮጵያውያን ለኢትዮጵያውያን” በተሰኘው የበጎ አድራጎት እንቅስቃሴ፣ ከ6 ሺ 500 በላይ ሕጻናት እርዳታ ማግኘታቸውን ጠቁመዋል።
በአዲስ አበባ ከተማ፣ አስኮ አካባቢ የተገነባው የሜሪጆይ ሆስፒታል ከ3 ወራት በኋላ እንደሚመረቅ የገለጹት ሲስተር ዘቢደር፤ ሆስፒታሉ ለ25 ሺ ታካሚዎች ነጻ የሕክምና አገልግሎት እንደሚሰጥ ተናግረዋል፡፡
በተጨማሪም፣ ከአሜሪካ የሲያትል ከተማ የነርሶች ማሕበር ለሜሪጆይ ኢትዮጵያ 18 የዳያሌሲስ ማሽኖች እንደተላኩ፣ በእነዚህም ማሽኖች አማካይነት ሐዋሳና አዲስ አበባ የኩላሊት ሕክምና ማዕከላት እንደሚከፈቱ ሲስተር ዘቢደር አክለው ጠቅሰዋል። በሌላ በኩል፣ ወጣት ባለሃብቶች የሚሳተፉበት ለሜሪጆይ ኢትዮጵያ አጋዥ የሆኑ የድጋፍ ስራዎችን የማስተባበር እንቅስቃሴ፣ ሐዋሳና አርባምንጭ ከተሞችን ጨምሮ በተለያዩ ከተሞች በቅርብ ቀናት ውስጥ እንደሚከናወን ተናግረዋል።

 ታዋቂዋ ድምጻዊት ቬሮኒካ አዳነ፣ የቤት እቃዎችን  ለገበያ የሚያቀርበው  የሚዲያ ኢትዮጵያ ብራንድ አምባሳደር ተደርጋ የተሾመች ሲሆን፤ በኢትዮጵያ ብቸኛው የሚዲያ የቤት እቃዎች አስመጪና ዋና አከፋፋይ ከሆነው ከኬ.መቅድም ጄነራል አስመጪና ላኪ ድርጅት ጋር የአጋርነት ስምምነት ፈጽመዋል፡፡
ባለፈው ረቡዕ  መጋቢት 10 ቀን 2017 ዓ.ም፣ ኬ.መቅድም አስመጪና ላኪ ድርጅት ከአርቲስት ቬሮኒካ አዳነ ጋር በመሆን በአጋርነት ስምምነታቸው ዙሪያ በስካይላይት ሆቴል ጋዜጣዊ መግለጫ ሰጥተዋል፡፡ አርቲስቷና ድርጅቱ በአጋርነት ለመሥራት የሚያስችላቸውን  የፊርማ ሥነስርዓትም አከናውነዋል፡፡
የሚዲያ ኢትዮጵያ ሥራ አስኪያጅ አቶ ሲሳይ በየነ በጋዜጣዊ መግለጫው ላይ በሰጡት ማብራሪያ፤ “ቬሮኒካ ድርጅታችንን የበለጠ ታስተዋውቅልናለች ብለን ብራንድ አምባሳደር አድርገን መርጠናታል፤ ማህበራዊ ሃላፊነታችንን ለመወጣትም አብረናት እንሰራለን፡፡” ብለዋል፡፡
የሚዲያ ብራንድ አምባሳደር በመሆኔ በጣም ዕድለኛ ነኝ ያለችው ድምጻዊት ቬሮኒካ፤ ስሙን ባላውቀውም የሚዲያን የቤት እቃዎች  መጠቀም የጀመርኩት ከሁለት ዓመት በፊት ነው ብላለች፡፡  “የምርቶቹን ጥራት በተመለከተ  እኔ ምስክር ነኝ፤ ተጠቅሜበት  አይቼዋለሁ” ስትልም ማረጋገጫ ሰጥታለች፡፡
ሚዲያ ኢትዮጵያ 12 ዘፈኖቿን ሙሉ ወጪውን ሸፍኖና የሚገባትን ክፍያ ፈጽሞ በጥራት እንዳሰራላት የገለጸችው ድምጻዊቷ፤ ይህም የአጋርነት ስምምነታቸው አካል መሆኑን ጠቁማለች፡፡
ባለፈው የፈረንጆች ዓመት በ”ፎርቹን 500”፣ በ227ኛ ደረጃ ላይ የተቀመጠው የቻይናው የቤት እቃዎች አምራች ሚዲያ፣ የማንችስተር ክለብ ኦፊሴላዊ አጋር ሲሆን፣ የክለቡ ተጫዋች ERLING HALLAND ደግሞ  የኩባንያው  ዓለማቀፍ ብራንድ አምባሳደር መሆኑ ይታወቃል፡፡
ኬ.መቅድም ላለፉት 8 ዓመታት ጥራት ያላቸው የሚዲያ የቤት ዕቃዎችን በብቸኝነት በማስመጣት ሲያከፋፍል የቆየ ሲሆን፤ ከእነዚህም መካከል ፍሪጆች፣ አየር ማቀዝቀዣዎች፣ የልብስ ማጠቢያ ማሽኖች፣ የውሃ ማከፋፊያዎች፣ እቃ ማጠቢያዎችና የውሃ ማጣሪያዎች ይገኙበታል፡፡ በተጨማሪም  ኬ.መቅድም፤ ከ30 ዓመታት በላይ  ሰሊጥ፣ የቅባት እህሎች፣ ጥራጥሬ፣ ቅመማቅመም፣ ጣሂኒ እና ቡና ለውጭ ገበያ ሲያቀርብ መቆየቱን ለማወቅ ተችሏል፡፡


“ለእናቴ”  የጽሁፍ ውድድር ለ10 ቀናት ተራዝሟል



          እናት ባንክ፤ የድካማቸውን ያህል ያልተነገረላቸውን ብዙኃን ኢትዮጵያውያን እናቶችን የሚወክል “እማዬ” የተሰኘ ቅርንጫፍ ከትላንት በስቲያ ሐሙስ  በይፋ ከፍቶ ሥራ ያስጀመረ ሲሆን፤ ቅርንጫፉ ልጆች ለእናቶቻቸው ልዩ ልዩ ፕሮግራሞችን በነፃ ማከናወን የሚችሉበት ነው ተብሏል፡፡
“እማዬ” የተሰኘው ቅርንጫፍ የተከፈተው ቅዱስ አቡነ ጴጥሮስ ሃውልት ፊት ለፊት በሚገኘው የቀድሞው የአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ የጋዜጠኝነትና ኮሙኒኬሽን ት/ቤት ህንጻ ላይ ሲሆን፤ የእናት ባንክ አመራሮች የቅርንጫፉን መከፈት አስመልክቶ ለጋዜጠኞች ማብራሪያ ሰጥተዋል፡፡
የእናት ባንክ ምክትል ፕሬዚዳንት ወ/ሮ ገነት ሃጎስ በሰጡት ማብራሪያ፤ “ባንኩ “እማዬ” የሚል ስያሜ የሰጠው ይኸው ቅርንጫፍ፤ በእናትነታቸው ብዙ ዋጋ የከፈሉ፣ ነገር ግን የልፋታቸውን ያህል ያልተጻፈላቸውና ያልተነገረላቸው እናቶች ውክልና እንዲኖራቸው ታስቦ የተከፈተ ነው፡፡” ብለዋል፡፡    
 “ልጆች ለእናቶቻቸው ልዩ ልዩ ፕሮግራሞችን በነጻ ማከናወን የሚችሉበት፣ ዲዛይኑም ሆነ በውስጡ ያሉት ግብዓቶች ብዙኃኑን የአገራችንን እናቶች እንዲወክል ታስቦ የተሰናዳ ነው፡፡” ሲሉም አክለዋል፤ምክትል ፕሬዚዳንቷ፡፡
ማንኛውም ሰው በቅርንጫፉ ተገኝቶ ስለ እናቱ ስሜቱን የሚገልጽበት እንዲሁም በእናቶች ዙሪያ የተጻፉ መጻህፍትን የሚያነብበትና ራሱም የሚጽፍበት ሥፍራ ተዘጋጅቷል ተብሏል፡፡
ይህ በእንዲህ እንዳለ፣ ጥር 30 ቀን 2017 ዓ.ም ይፋ የሆነው “ለእናቴ” የተሰኘ የፅሁፍ ውድድር መጠናቀቁን የጠቀሰው ባንኩ፤ የ”እማዬ” ቅርንጫፍ መከፈትን ምክንያት በማድረግ ውድድሩን ለቀጣዮቹ አስር ቀናት ማራዘሙን አስታውቋል፡፡
ለ”እናቴ” የተሰኘው የጽሁፍ ውድድር ሁሉም ሰው ለእናቱ ያለውን ፍቅር፣ አክብሮት፣ ውለታና ምስጋና በዝርው ጽሁፍ (ግጥም ያልሆነ፣ በወግ መልክ፣ በደብዳቤ ቅርጽ) የሚያቀርብበት ሲሆን፤ “የዓመቱ ድንቅ እናት” የተሰኘው ውድድር ደግሞ ተወዳዳሪዎች በአካባቢያቸው በሕይወት ያሉና የሚያውቋቸውን ወይም የራሳቸውን እናቶች በጽሁፍ በድምጽና በምስል ቀርጸው በቀጥታ የሚሳተፉበት ነው፡፡
አዲስ አበባ የሚገኙና በውድድሩ መሳተፍ የሚፈልጉ በአዲሱ “እማዬ” ቅርንጫፍ እንዲሁም በክልሎች ያሉ ተወዳዳሪዎች በአቅራቢያቸው በሚገኙ የባንኩ ቅርንጫፍ ሥራዎቻቸውን ማስገባት ይችላሉ ተብሏል፡፡
የዘንድሮ የጽሑፍ ውድድር የመዝጊያ መርሃ-ግብር፣ የእናቶች ቀን በሆነው የግንቦት ወር መጀመሪያ፣ በደማቅ ሥነ-ስርዓት እንደሚካሄድ ባንኩ አስታውቋል፡፡    
በመላ ሃገሪቱ “እማዬ” ቅርንጫፍን ሳይጨምር 206 ቅርንጫፎች ያሉት እናት ባንክ፣ በአዲስ አበባ የሚገኙ ቅርንጫፎቹን ለሃገርና ለወገን በጎ በዋሉና  ዝናን ባተረፉ እንስቶች ስም ሲሰይም መቆየቱን አስታውሶ፣ ወደፊትም ቅርንጫፎቹን በመሰል እንስቶች ስም መሰየሙን  እንደሚቀጥልበት  ጠቁሟል፡፡

 “ደንቡን መተላለፍ ከ2ሺ ብር እስከ አንድ ሚሊዮን ብር ያስቀጣል!”


      አዲስ አበባ ለመመስረቷ ምክንያት ከሆኗት ወሳኝ ምክንያቶች መካከል ማራኪና ተስማሚ ውበቷ እንዲሁም የተፈጥሮ ሃብቷ ይጠቀሳሉ፡፡ ከእነዚህ የተፈጥሮ ጸጋዎች መካከል ደግሞ  ዓመቱን ሙሉ ይፈሱ የነበሩ ንጹህ ወንዞቿ ይገኙበታል፡፡
በጊዜ ሂደት ከህዝብ ቁጥር መጨመርና ከከተሜነት መስፋፋት ጋር ተያይዞ ወደ ወንዞች በሚለቀቁ ቆሻሻዎች እንዲሁም የተለያዩ ተረፈ ምርቶችና የኢንዱስትሪ ፍሳሾች ሳቢያ ለመዝናኛ ጭምር ያገለግሉ የነበሩት የመዲናዋ ንጹህ ወንዞች በእጅጉ ተበክለው ለዕይታም ለጤናም አደገኛ እየሆኑ መጥተዋል፡፡ የወንዞቹ መበከል የከተማ ግብርና ላይ ለተሰማሩ አርሶአደሮችም  ትልቅ ተግዳሮት መደቀኑ ይነገራል፡፡  
ባለፉት 20 ዓመታት የአዲስ አበባ ህዝብ ቁጥር እንደ ሌሎች የአፍሪካ ከተሞች ሁሉ ከእጥፍ በላይ እንዳደገ  መረጃዎች ይጠቁማሉ፡፡ ባለፉት ጊዜያት ዝናብ በዘነበ ቁጥር  የመዲነዋ ወንዞች መሀል ከተማዋን በጎርፍ የሚያጥለቀልቁ ሲሆን፤ ጎርፉ ተሸክሞት የሚመጣው ቆሻሻም  የነዋሪውን ጤና ለአደጋ ይዳርጋል፡፡ የመዲናዋን ንጽህናም ይበክላል፡፡
በመዲናዋ የሚገኙ ወንዞች ለበርካታ ዓመታት ትኩረትና ጥበቃ ተነፍጓቸው በመቆየታቸው   ለነዋሪው ጥቅምና ውበት ከመሆን ይልቅ ጉዳትና ጠንቅ ሆነዋል፡፡ እንኳንስ የመዝናኛ ሥፍራና የቱሪዝም ማዕከል ሊሆኑ ቀርቶ፣ በይፋ የቆሻሻና ፍሳሽ መልቀቂያና ማከማቻ ተደርገው መቆየታቸው ይታወቃል፡፡ ይሄ  ደግሞ በአፍሪካ መዲናነቷና በዓለማቀፍ ተቋማት መቀመጫነቷ ለምትታወቀው አዲስ አበባ ፈጽሞ የሚመጥናት አይደለም፡፡    
 በህገ መንግሥቱ አንቀፅ 44 ንኡስ አንቀፅ 1 ላይ በግልፅ እንደተቀመጠው፤ ሁሉም ሰው ንፁህና ጤናማ በሆነ አካባቢ የመኖር መብት ያለው ሲሆን፤ የተሻሻለው የአዲስ አበባ ቻርተር 361/1995 ህግም ይህንኑ ይደነግጋል፡፡ ምንም እንኳን ከ23 ዓመት በፊት የወጣ የብክለት መከላከል አዋጅ ህግ ቢኖርም፣ በትግበራው ላይ በነበረው ክፍተት ሳቢያ ውጤታማ ሳይሆን መቅረቱ ይታወቃል፡፡ በዚህም የተነሳ የመዲናዋ ወንዞች እጅጉን ቆሽሸውና ተበክለው አደገኛ የጤና ጠንቅ እንዲሆኑ አድርጓቸዋል፡፡     
ከጥቂት ዓመታት በፊት ታዲያ በጠ/ሚኒስትር ዶ/ር ዐቢይ አህመድ ሃሳብ ጠንሳሽነት፣  አዲስ አበባን እንደ ስሟ ለማስዋብና ለማዘመን እንዲሁም ከአፍሪካ ተመራጭ መዲና ትሆን ዘንድ   ያለመ የወንዝ ዳር ልማት ፕሮጀክት ተቀርጾ  በይፋ መተግበር ጀምሯል፡፡
የአዲስ አበባ የወንዝ ዳር አረንጓዴ ልማት ፕሮጀክት፣ ወይም “ሸገርን የማስዋብ ፕሮጀክት” እ.ኤ.አ በየካቲት ወር 2019 ዓ.ም በይፋ  የተጀመረ ሲሆን፤ ዓላማውም በዋናነት የከተማዋን ወንዞች በማጽዳት አረንጓዴና ውብ የህዝብ መዝናኛ ሥፍራ መፍጠር ነው፡፡ ፕሮጀክቱ በአጠቃላይ 56 ኪ.ሜ የሚረዝም ሲሆን፤ ከእንጦጦ ተነስቶ አቃቂ የፍሳሽ ማጣሪያ ጣቢያ ይደርሳል፡፡
በአሁኑ ወቅት የወንዝ ዳርቻ ልማት ፕሮጀክቱ የመዲናዋን ወንዞች ወደ ቀድሞ ተፈጥሯዊ ማንነታቸው ለመመለስና የመዝናኛና የቱሪዝም ማዕከል ለማድረግ ታልሞ በትጋት እየተሰራ ይገኛል፡፡ ለአብነትም በከተማው አስተዳደር በ2ኛ የኮሪደር ልማት ፕሮጀክት ስራዎች ከሚለሙ 8 ኮሪደሮች መካከል 21.5 ኪ.ሜ እርዝመት ያለው የእንጦጦ-ፒኮክ ወንዝ ዳርቻ ልማትና 20 ኪ.ሜ የሚረዝመው የቀበና ወንዝ ዳርቻ ልማት ተጠቃሽ ናቸው፡፡   
ፕሮጀክቱ በወንዝ ዳርቻዎች ላይ ስር የሰደደ ችግር ለሚታይባት አዲስ አበባ መሰረታዊ ለውጥ እንደሚያመጣም በከተማ አስተዳደሩ ጭምር ታምኖበት በቁርጠኛ አቋምና ትጋት ቀን ከሌት እየተሰራ ይገኛል፡፡
በከተማዋ እየተከናወነ የሚገኘው 2ኛው የኮሪደር ልማት ፕሮጀክት  አንድ አካል የሆነው የወንዝ ዳርቻ ልማት፤ መዲናዋ የተፈጥሮ ፀጋዎቿን በአግባቡ ለመጠቀም በሚያስችል መልኩ ወንዞቿን ፅዱና አረንጓዴ በማድረግ፣ ለራሷም ሆነ ለተቀረው ዓለም አርአያ  ለመሆን ታይቶ በማይታወቅ የለውጥ ጉዞ ላይ ትገኛለች፡፡
ይሁን እንጂ አሁንም አንዳንድ ግለሰቦችና ድርጅቶች ደረቅ ቆሻሻዎችና የኬሚካል ፍሳሾችን ወደ ወንዞች በመልቀቅ የወንዞችን ብክለት እንዲባባስ እያደረጉ ናቸው። የብክለት መጠኑ ከላይኛው ተፋሰስ ወደ ታችኛው ተፋሰስ እየጨመረ በመምጣቱ በማህበረሰቡ ላይ ከፍተኛ የጤና መታወክን እያስከተለ ይገኛል።
በዚህም ምክንያት በህገ-መንግሥቱ የተቀመጠውን መብትና ግዴታ መፈፀም የግድ ብቻ ሳይሆን ወቅቱ የሚጠይቀው አሳሳቢ ጉዳይ በመሆኑ የማህበረሰቡን ጤና የሚያውኩና የወንዞችን ብክለት የሚያባብሱና ሌሎች መሰል ተግዳሮቶችን መፍታት አስፈላጊ ሆኖ ተገኝቷል። ወንዞችን ማልማትና ከብክለት መከላከል ካልቻልን አዲስ አበባን የማስዋብና ማዘመን ራዕያችንን እውን ማድረግ አይታሰብም፡፡
የወንዞችን ደህንነት ለመጠበቅና ከብክለት ለመከላከል በአስተዳደሩ እየተከናወነ ከሚገኙ የወንዞች ዳር ልማት ጎን ለጎን፣ አዲሱ የወንዞች ዳርቻ ብክለት መከላከል ደንብ ቁጥር 180/2017 በአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ካቢኔ ፀድቆ፣ ከታህሳስ 4 ቀን 2017 ዓ.ም ጀምሮ ተግባራዊ ተደርጓል፡፡
ደንቡን በተገቢው ሁኔታ ተረድቶ ተግባራዊ ማድረግ ይቻል ዘንድ በተለያዩ ጊዜያት በርካታ የግንዛቤ ማስጨበጫ የውይይት መድረኮችን በመፍጠር ከማህበረሰቡ ጋር መግባባት ላይ የተደረሰ ሲሆን፤ አሁንም የግንዛቤ ማስጨበጥ ስራው ይበልጥ ተጠናክሮ መቀጠል እንዳለበት በመታመኑ በወንዞች ዳርቻ አካባቢ ለሚገኙና ከጉዳዩ ጋር በቀጥታ ግንኙነት ያላቸው አምራችና አገልግሎት ሰጪ ተቋማት በደንቡ ዙሪያ በቂ ግንዛቤ እንዲጨብጡ እየተደረገ ነው፡፡
በከተማው የሚገኙ ወንዞች ለከተማዋ የውበት ምንጭ ሳይሆኑ የቆሻሻ መጣያ ሆነው መቆየታቸውን የሚናገሩት የአዲስ አበባ ከተማ አካባቢ ጥበቃ ባለስልጣን ዋና ሥራ አስኪያጅ አቶ ዲዳ ድሪባ፤ ይህ ታሪክ እንዲቀየር አስተዳደሩ በርካታ ሥራዎችን በመሥራት ላይ እንደሚገኝ ይገልጻሉ፡፡
ከተማችን ከግብር ከፋዮች በምታገኘው ገቢ የኮሪደር ልማትን ጨምሮ በርካታ ፕሮጀክቶችን በማከናወን ላይ እንደምትገኝ የጠቁሙት ዋና ሥራ አስኪያጁ፤ እነዚህን የለሙና የተገነቡ ስፍራዎች ለመጠበቅ የተለያዩ ደንቦች ጸድቀው ወደ ትግበራ መገባቱን ይናገራሉ፡፡
የአዲስ አበባ ከተማ ወንዞች ብክለት በአካባቢና በጤና ላይ የሚያደርሰው ጉዳትና  መፍትሔዎች እንዲሁም የወንዞች ዳርቻ ልማትና ብክለትን ለመከላከል በወጣው ደንብ ቁጥር 180/2017 እና የቅጣት ሰንጠረዥ ዙሪያ ከማህበረሰቡ ጋር በስፋት ውይይት ተደርጎበት የጋራ መግባባትና  ግንዛቤ ላይ መደረሱን አቶ ዲዳ ድሪባ አብራርተዋል፡፡
በአሁኑ ወቅትም  ከግንዛቤ ማስጨበጥ ሥራው ጎን ለጎን፣ ደንቡን ተላልፈው በሚገኙ አካላት ላይ አስተዳደራዊ እርምጃ መወሰድ መጀመሩን ነው ዋና ሥራ አስኪያጁ የገለጹት፡፡
በአስተዳደሩ ካቢኔ በጸደቀው አዲሱ የወንዞች ዳርቻ ብክለት መከላከል ደንብ መሠረት፣ ደንቡን ተላልፈው በሚገኙ ግለሰቦችና ተቋማት ላይ የገንዘብ ቅጣት የሚጣል ሲሆን፤ ዝቅተኛው የገንዘብ ቅጣት ሁለት ሺህ ብር፣ ከፍተኛው ደግሞ እስከ አንድ ሚሊዮን ብር እንደሚደርስ  በሰነዱ ላይ  ተመላክቷል።
የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ደንብ ማስከበር ባለስልጣን ዋና ሥራ አስኪያጅ ሻለቃ ዘሪሁን ተፈራ ባስተላለፉት መልዕክት፣ንፁህ ወንዝና ጤናማ አካባቢ ለመፍጠር በሚደረገው ጥረት፣ ማህበረሰቡም ሆነ ተቋማት ሃላፊነታቸውን በአግባቡ በመወጣት፣ ከአስተዳደሩ ጎን እንዲቆሙ ጥሪ አቅርበዋል፡፡
ወደፊትም ለህብረተሰቡ የግንዛቤ ማስጨበጥ ስራው ተጠናክሮ የሚቀጥል ሲሆን፤ ደንቡን ተላልፈው በሚገኙ ግለሰቦችና ተቋማት ላይ አስተዳደራዊ እርምጃ መውሰድ መጀመሩም አስታውቀዋል፡፡

አንዳንድ ተረቶች በአንድ ወቅት አልደመጥ ሲሉ፣ በሌላ ወቅት ተደግመው መነገራቸው ግድ ይሆናል፡፡ የሚከተለውም እንደዚያው ነው፡፡
ከእለታት አንድ ቀን ሦስት አህዮች በጠፍ ጨረቃ ሰፊ መስክ ላይ እየጋጡ ሳሉ፤ ሦስት ጅቦች የሚበላ ፍለጋ ሲዘዋወሩ ያገኙዋቸዋል፡፡
ጅቦቹ ገርሟቸዋል፡፡
አንደኛው ጅብ፤
“እነዚህ አህዮች እንዴት ቢጠግቡ ነው በእኛ ሰዓት፤ በእኛ ግዛት እንደዚህ ተዝናንተው የሚግጡት?”
ሁለተኛው ጅብ፤
“እውነትም የሚገርም ነው፡፡ የተማመኑት ነገር ቢኖር ነው እንጂ እንዲህ ያለ ድፍረት አይፈጽሙም ነበር”
ሦስተኛው ጅብ፤
“ታዲያ ለምን ችሎት ተቀምጠን አንፈርድባቸውም?” ሲል ሃሳብ አቀረበ፡፡
አህዮቹን ከበቡና ተራ በተራ ሊጠይቋቸው ተሰየሙ፡፡
የመጀመሪያዋን አህያ ጠሩና ጠየቋት፡፡ የማህል ዳኛው ነው የሚጠይቃት፡፡
“እሜቴ አህያ፤ ለመሆኑ በእኛ ሰዓት፣ በእኛ ግዛት፣ በጠፍ ጨረቃ፣ እንዲህ ዘና ብለሽ የምትግጪው ማንን ተማምነሽ ነው?”
እሜቴ አህያ፤
“አምላኬን፣ ፈጣሪዬን ተማምኜ ነው፡፡ በእኔ ላይ ግፍ የሚሰራን አምላኬ ዝም አይለውም፡፡ መአት ያወርድበታል፡፡”
የማህል ዳኛው ጅብም፤
“መልካም ሂጂ፡፡ ፍርድሽን ትሰሚያለሽ፡፡ ሌላዋን ጥሪያት”
ለሁለተኛዋ አህያም ጥያቄው ቀረበላት፤
“አንቺስ ማንን ተማምነሽ ነው በጠፍ ጨረቃ፣ በእኛ ሰዓት፣ በእኛ ግዛት
ፍንጥዝጥዝ ብለሽ የምትግጪው?”
ሁለተኛይቱ አህያም፤
“ጌታዬን፣ አሳዳሪዬን ተማምኜ ነው፡፡ በእኔ ላይ ጥቃት የሚያደርስን ማንምም ቢሆን ጌታዬ አይምረውም፡፡ ይበቀልልኛል ብዬ በማመን ነው” ስትል መለሰች፡፡
ማህል ዳኛው ጅብ፤
“መልካም፡፡ አንቺም ፍርድሽን ትሰሚያለሽ፡፡ ሌላዋን ጥሪያት” አላት፡፡
ሦስተኛይቱ ቀረበች፡፡
ማህል ዳኛ ጅብም፤
“አንቺስ ማንን ተማምነሽ ነው ይሄ ሁሉ መዝናናት?” አላት
ሦስተኛይቱ አህያም፤
“እናንተን፣ እናንተን፣ የአካባቢውን ገዢዎች ተማምኜ ነው ጌቶቼ”
ዳኛውም፤
“መልካም፡፡ ሁላችሁም ፍርዳችሁን ጠብቁ” አሉና ሸኟት፡፡
ዳኞቹ መምከር ጀመሩ፡፡
ግራ ቀኝ ዳኞች አስተያየት ከሰጡ በኋላ፣ የማህል ዳኛው ጅብ እንዲህ አሉ፡-
“የመጀመሪያዋን ብንበላት እንዳለችው አምላክ አይለቀንም፡፡ ይበቀልላታል፡፡ ሁለተኛዋን ብንበላት ምናልባት አሳዳሪ ጌታዋ ተከታትሎ ያጠፋናል፡፡ ይቺን ሦስተኛዋን እኛን የተማመነችውን ብንበላት ማናባቱ ይጠይቀናል!?”  ሲል መሪ - ሀሳብ አቀረበ፡፡
ሁለቱ ጅቦች ባንድ ድምጽ፤
“እውነት ነው፡፡ እኛን የተማመነችውን እንብላት!” አሉ፡፡
እነሱን የተማመነችው ላይ ሰፈሩባት፡፡
***
የጌቶች አስተሳሰብ ምን እንደሚመሰል ተገዢ ወዳጆች ማወቅ አለባቸው፡፡ ሎሌነቱን በቅጥ አለመያዝ የመጨረሻውን ቀን ከማፋጠን አያልፍም፡፡ “የምጣዱ እያለ የእንቅቡ ተንጣጣ” የሚለውን ተረት፣ በአፉ የሚንጣጣ ሁሉ በጊዜ ሊገነዘብ ይገባል፡፡ መጨረሻው፤ “ያመኑት ፈረስ ይጥል በደንደስ” ነውና፡፡ “እናቴን ያገባ  ሁሉም አባቴ ነው” ለሚሉ የዋሀን ሁልጊዜ ፋሲካ ሊመስላቸው ቢችልም፣ ለሁሉም ጊዜ አለውና “ምነው ምላሴን በቆረጠው” የሚያሰኝ የፍርድ ቀን እንደሚኖር አሌ አይባልም፡፡ “እንብላም ካላችሁ እንብላ፣ አንብላም ካላችሁ እንብላ” በሚል ጅባማ ፍልስፍና ውስጥ መበላላት መሪ መርሀ-ግብር መሆኑን ለአፍታም መዘንጋት የለበትም፡፡
“ለጋማማ አህያም ጋማ አላት
አያስጥልም እንጂ ጅብ ሲዘነጥላት” ሲባል የከረመው ያለ ነገር አይደለም፡፡
“እነሆ ብዙ ዘመን አለፍን፡፡ ከሁሉም የተረፈን ብዙ ምላሶችና እጅግ ጥቂት ልቦች ናቸው” ይላል ሲጆርጅ የተባለው ፀሀፊ፡፡ በሀገራችን በቅንነት ሃሳብ የሚሰጡና በሎሌነት ሀሳብ የሚሰጡ መለየት አለባቸው፡፡ “ውሸት አለምን ዞሮ ሊጨርስ ሲቃረብ እውነት ገና ቦት ጫማውን እያጠለቀ ነው” መባሉ በምክንያት እንጂ በአቦ - ሰጡኝ አይደለም፡፡ በየአገሩ፤ የንጉስ አጫዋቾች የተለያዩ ናቸው፡፡ አንድ የጋራ ባህሪ ግን አላቸው - ንጉሱ ሲያስነጥሱ ማስነጠስ፡፡ አድር ባይነት፡፡ በመካያው ራሱ አድርባዩ ማንነቱ ይጠፋበትና፤ “የዘሬን ብለቅ ያንዘርዝረኝ” ማለት እንኳ ይሳነዋል፡፡ “ነገር አንጓች እንኳን ለጌታው ለራሱም አይመችም” ነውና ፍፃሜው አጓጉል መሆኑ እሙን ነው፡፡
የትእዛዝ ሁሉ ጉልላት ለህሊና መታዘዝ ነው፡፡ ማንም ቢሆን ማን፤ ህሊናውን ሲክድ አታላይ መሆኑ አይቀሬ ነው፡፡ ብልጥ ለማኝ፤ “ጌታዬ ጌታዬ፣ አምና የሰጡኝን ልብስ አምስት ዓመት ለበስኩት” እያለ ይኖራል፡፡ በእውቀት ያልተደገፈ ድፍረት፤ የህሊና ማጣት ምርኩዝ ነው፡፡ ወትሮም “መራዡ ተኳሹ” ሲል የኖረ፣ “በራዡ ከላሹ” ማለት ከጀመረ ሁለተዜ ጥፋት ነው፡፡ ሀገራችን አያሌ አድር - ባይ አይታለች፡፡ ለሀገራችን ጎታቿም አጥፊዋም “አሾክሹዋኪው” ነው፡፡ ከታሪክ መማር እርም በሆነባት አገር፣ ቀለሙን እየለዋወጠ አድር - ባይ  ሁሉ እየመጣ፤ “እንቅፋት በመታው ቁጥር ቲዎሪ ድረስ (ያውም እውነተኛ ቲዎሪ ካለው) እያለ፤ “መንገድ ባስቸገረው ቁጥር “መመሪያ ማሪኝ” እያለ ህሊናውን እየሸጠ ይኖራል፡፡ ልባም አይደለምና አፍ ያወጣል፡፡ ምላሹ እየረዘመ፣ አንጎሉ እየጨለመ ይሄዳል፡፡ አበው “ከመሃይም ምላስ ይሰውረን” የሚሉት ለዚህ ነው፡፡ ማህታማ ጋንዲ እንግሊዝን “በመጨረሻ ባዶህን ትወጣለህ!” ማለቱን አንርሳ፡፡
“ቅዳሴ ሲያልቅበት ቀረርቶ አከለበት” እንዲሉ፣ በምላሱ የሚተዳደር ሰው፣ ውሸት ማብዛቱ ግዱ ነው፡፡ እውቀተ - ቢስ መሰረቱ ለእውነት ረሃብ ያጋልጠዋል! “አፈኛ ሴት፣ የአምስት ዳኛ ሚስት ነኝ፤ ትላለች” የሚለው የወላይታ ተረት ኢላማ ይሆናል፡፡



Page 5 of 765