Administrator

Administrator

በአገራችን አዲስ አበባ የተገነባው ዓለም አቀፍ ኤግዚቢሽን እና የኮንቬንሽን ማዕከል ከቱሪዝም ገቢ በተጨማሪም፣ የኤግዚቢሽንና የጉባኤ ማዕከል በርካታ ጥቅሞችን ያበረክታል። በዙሪያው የቢዝነስና የስራ ዕድሎችን የሚያስፋፋ፣ የእድገትና የብልጽግና ግንኙነቶችን የሚፈጥር የኢኮኖሚ መነሃሪያ (Hub) በመሆን ያገለግላል። ባሕላዊ፣ ጥበባዊና ማኅበራዊ ፋይዳዎችን የሚያበራክትም ነው - የሚሰጣቸው አገልግሎቶች በዓይነታቸው ብዙ ናቸው።
የኢንዱስትሪ፣ የቴክኖሎጂ፣ የምርትና የአገልግሎቶች ዓለም አቀፍ ኤግዚቢሽን ሲዘጋጅ፣ የዕውቀት ሽግግርን ያቀላጥፋል። የኢንቨስትመንትና የቢዝነስ አማራጮችን ይከፍታል። የንግድና የገበያ ግንኙነቶችን ለመፍጠር፣ ውል ለመፈራረም፣ ሽያጭና ግዢ ለመጀመር መልካም አጋጣሚዎችን ይፈጥራል።
ዓለም አቀፍ ጉባኤዎችንና ዝግጅቶችን የሚያስተናግድ አገር፣ በዓለማቀፍ የዲፕሎማሲና ኢኮኖሚ መድረክ ተሰሚነቱ ይጨምራል። የኢኮኖሚ ድርሻው  እያደገ ይሄዳል።
አዲስ አበባ የኤግዚቢሽንና የኮንቬንሽን ማዕከል ያስፈልጋታል። ለዚያውም፣ በዓለማቀፍ ደረጃ መወዳደርና ተመራጭነትን ማግኘት የሚችል፣ በላቀ የጥራት ደረጃ አስፈላጊ አገልግሎቶችን የሚሰጥ ማዕከል እንደሆነ ከንቲባ አዳነች አበቤ ይናገራሉ።
አዲስ ዓለማ ዓቀፍ ኤግዚቢሽንና ኮንቬንሽን ማዕከል፤ 5ሺ እና 2ሺ ተሳታፊዎችን የሚያስተናግዱ ትልልቅ አዳራሾች ፣ ለኤግዚቢሽኖች እንዲሁም ለጉባኤዎች በስምንት ንዑስ አዳራሽ በርካታ ስብሰባዎችን በአንድ ጊዜ ማስተናገድ የሚያስችል ነው። በዓለም የኤግዚቢሽንና የኮንፈረንስ ቱሪዝም ካርታ ላይ የኢትዮጵያ ስምና ድርሻ ጎልቶ እንዲታይ የሚያደርግ ሰፊ ፕሮጀክት። ከተጓዳኝ ግንባታዎች ጋር 15 ሄክታር ይሸፍናል። በዓለም ደረጃ የመወዳደርና ተመራጭነትን የማግኘት ብቃት እንዲኖረው ታስቦ የተገነባ።


መዲናችን አዲስ አበባ ዓለም ዓቀፍ ኤግዚቢሽኖችን፣ ጉባኤዎችንና ስብሰባዎችን በአንድ ማዕከል የማስተናገድ አቅም አልነበራትም፤ ይህን የአገራችንን ጉድለት የሚያሟላ ማዕከል ተገንብቶ ለምርቃት የደረሰ ፕሮጀክት፤ ለከተማችንና ለአገራችን ተጨማሪ የስበት ማዕከል ይሆንልናል።
በመሀል ከተማ የዓድዋ ድል መታሰቢያ ግንባታ፣ ከአኩሪ ታሪካችን ጋር የተያያ ጥሩ ነገር ፈጥሮልናል።
የትልቅ ታሪክ መዘክር ከመሆኑም በተጨማሪ፣ በግንባታው ጥራትና ውበት፣ በጠቅላላ ይዘቱና በተሟላ አገልግሎቱ ምን ያህል ተመራጭነትን እንዳገኘ በተግባር አይተናል። የኮንፈረንስ ቱሪዝም ስበት ለመሆን ችሏል። አዲስ አበባ የዓለም ዓቀፍ ኤግዚቢሽኖችና ጉባኤዎች መነሃሪያነቷን የምናረጋግጥበት፣ የኮንፈረንስ ቱሪዝም ማዕከልነቷን በኩራት የምንመሰክርበት ይሆናል።
አገራችን የተባበሩት መንግስታት ድርጅት መሥራችም ናት። የተመድ የአፍሪካ ኢኮኖሚክ ኮሚሽን የሚገኘው በአዲስ አበባ ነው። ከዚህም ጋር ተያይዞ በርካታ የተመድ ተቋማት በአዲስ አበባ ከትመዋል። ይሄ ሌሎች አገራት የማያገኙት ዕድል ነው። የዓለም የዲፕሎማሲ ማዕከላት ተብለው የሚጠቀሱ የዓለማችን አገራት በጣት የሚቆጠሩ ናቸው። ኢትዮጵያ ከእነዚህ መካከል አንዷ ናት።
በታሪካዊ ሀብቶችና በተፈጥሮ ጸጋዎች የታደለች ቢሆንም ግን፣ በዓለም ዓቀፍ የቱሪዝምና የኢኮኖሚ ዘርፍ ውስጥ ተገቢውን ጥቅምና ድርሻ እያገኘች አይደለችም። በተመድና በአፍሪካ ሕብረት ስር የተካተቱ ብዙ ተቋማት በከተማችን አሉ። ዓለም ዓቀፍ ኤግዚቢሽኖችንና ጉባኤዎችን ማካሄድ ይፈልጋሉ። እዚሁ አገራችን ውስጥ ቢሆንላቸው ይመርጣሉ - ብዙዎቹ። ነገር ግን፣ ተስማሚ ማዕከላትና አማራጮች ፍለጋ ወደ ሌሎች አገራት ያማትራሉ።
ትልልቅ ዓለም ዓቀፍ ኤግዚቢሽኖችን በብቃት ለማስተናገድ የምንችልበት፣ ዓለም ዓቀፍ ደረጃውን የጠበቀ አገልግሎት የሚሰጥና ዘመናዊ መሠረተ ልማቶች የተሟሉለት ማዕከል በብቃት ሳናሰናዳ ስለቆየን በየዓመቱ ብዙ ዕድሎችን ያስቀርብናል። የአገራችንን ኢኮኖሚ ሊያሳድጉ የሚችሉ የሥራና የገበያ፣ የኢንቨስትመንትና የቱሪዝም ዕድሎች ዓይናችን እያየ ያመልጡን ነበር። አሁን ግን በዓለም ዓቀፍ ደረጃ ጥራቱን የጠበቀና የተሟላ አገልግሎት የሚሰጥ ማዕከል ተገንብቷል።
የማዕከሉ ዋና ሥራ አስፈጻሚ አቶ ሲሳይ ገመቹ እንደሚሉት፣ የግንባታውን ጥራትና ውበት በርካታ ባለ ሙያዎች አይተው መስክረውለታል።
ትልቁ ሁለገብ አዳራሽ - ለስብሰባም ለኤግዚቢሽን ማሰናጃም የሚሆንና 5 ሺ ተሳታፊዎችን ማስተናገድ የሚችል ነው፡፡
ዲዛይኑ የሕንጻውን ንድፍ በግላጭ የሚያሳይ “ስቲል ስትራክቸር” እንደሆነ ጠቅሰው፣ በባለ ሙያዎችም ሆነ በተመልካቾች ዐይን ሲታይ ያምራል ብለዋል። ለእያንዳንዱ የስብሰባ ወይም የኤግዚቢሽን ይዘት በሚስማማ መንገድ አዳራሹን ለማስጌጥ እንዲያመች ታስቦበት የተሠራ እንደሆነም ገልጸዋል።
በርካታ ሺ ሰዎችን በአንዴ የሚያስተናግድ ሰፊ አዳራሽ ቢሆንም፣ አየር እንደ ልብ ስለሚያንሸራሽር፣ የጣሪያው ከፍታም 28 ሜትር ስለሆነ የሙቀት መቆጣጠሪያ አያስፈልገውም። በተፈጥሯዊ ብርሃን አዳራሹን የሚያጥለቀልቁ ረዣዥምና ሰፋፊ መስኮቶች አሉት። የፊልም ምስሎችን ለማየት ወይም የኤሌክትሪክ መብራት መጠቀም ካስፈለገም፣ መስኮቶቹን ሙሉ ለሙሉ መጋረድ ይቻላል።
ሁለት የምግብ አቅርቦት ማስተናገጃ ስፍራ፣ እንዲሁም የእረፍት ሰዓት የሻይ የቡና መስተናገጃ ሰፊ ቦታ አለው። ከአዳራሹ ሥር በታችኛው ፎቅ ወደ ተዘጋጁት በርካታ የመጸዳጃ ቤቶች የሚያደርስ መተላለፊያ የሚገኘውም በዚሁ አቅጣጫ ነው። በአዳራሹ ሌላኛው ጎን የክብር እንግዶች መቆያ ቦታና ተጨማሪ የመጸዳጃ አገልግሎት ስፍራዎች ተሰርተውለታል።
የኤግዚቢሽን አዳራሽ - በ5 ሺ ካሬ ሜትር ስፋት የተገነባ፣ ከሁለገብ አዳራሽ ቀጥሎ ከላይ የምናገኘው ትልቅ አዳራሽ ዋና አገልግሎቱ ለኤግዚቢሽን ነው።
መካከለኛ አዳራሽ - አንድ ሺ ሰዎችን ያስተናግዳል። ዘና ያለ መንፈስ እንዲኖረው፣ አየር በደንብ እንዲንሸራሸር፣ የተፈጥሮ ብርሃን በሰፊው እንዲያስገባ ታስቦበት የተሰራው አዳራሽ፣ ጣሪያው 28 ሜትር ቁመት አለው።
ከመደበኛ የኤሌክትሪክ መስመሮች በተጨማሪ ወለል ሥር የተቀበሩ መስመሮችም ተዘርግተውለታል። ኤግዚቢሽን የሚያቀርቡ ተሳታፊዎች፣ ከአዳራሹ ወለል ላይ ከዳር እስከ ዳር የኤሌክትሪክ ሶኬቶችን በአጠገባቸው ስለሚያገኙ፣ ግራ ቀኝ የሚዝረከረኩ ገመዶች አይኖሩም።
ከአንድ አቅጣጫ በኩል፣ ከአዳራሹ አጠገብ የመጋዘን ክፍሎች አሉት። በሌላኛው አቅጣጫ ደግሞ ቢሮዎችን ይዟል። በአጠቃላይ ከኤግዚቢሽን ዝግጅት ጋር የተዛመዱ  አገልግሎቶችን ሁሉ እንዲያሟላ ተድርጎ ነው የተሠራው።
ሰፊ የትዕይንት አዳራሽ - በተገጣጣሚ ግድግዳም ሲከፋፍሉት ደግሞ ሰባት ንዑስ አዳራሾች ያሉት ሲሆን አራተኛ ፎቅ ላይ የምናገኘው ሰፊ አዳራሽ፣ 2 ሺ ሰዎችን ማስተናገድ ይችላል። ለትልቅ ጉባኤ ሊያገለግል ይችላል።
ስዕሎችን ለማሳየት ወይም ሌላ ለእይታ የሚቀርቡ ድግሶችን ለማዘጋጀትም የአዳራሹ ቅርጽ ይመቻል። ተመልካቾች በአንዱ ጫፍ ገብተው፣ በእይታ ድግሶች ተስተናግደው ዓይናቸውን ረክቶ በሌላኛው ጥግ ይወጣሉ። ካስፈለገ ደግሞ ረዥሙ አዳራሽ ውስጥ ተገጣጣሚ ግድግዳዎች ተዘርግተው፣ ለንዑስ ስብሰባዎች የሚያገለግሉ 7 መካከለኛና አነስተኛ አዳራሾች ይወጣዋል።
ግድግዳዎቹ ተጣጣፊ ተገጣጣሚ ቢሆኑም፣ ከመደበኛ ግድግዳ አይተናነሱም። ድምጽ አያሳልፉም፤ ሲታዩም ያምራሉ ብለዋል - የማዕከሉ ዋና ስራ አስፈጻሚ።
አዳራሹ አራተኛ ፎቅ ላይ ቢሆንም፣ ከበቂ በላይ መተላለፊያዎች አሉት። በየአቅጣጫው በተሠሩ በርካታ ሰፋፊ ደረጃዎች አማካኝነት መግባትና መውጣት ይቻላል። ከደረጃዎች ጎን “ስካሌተሮች” አሉ። ከእነዚህ በተጨማሪም አሳንሰሮች (ሊፍቶችን) መጠቀም ይቻላል። መጨናነቅም ሆነ መጣበብ አይኖርም።
የአዳራሾቹን አገልግሎት በትክክል ለማከናወንና ለመቆጣጠር የሚያገለግሉ የቴክኒክና የቴክኖሎጂ ክፍሎችን ጨምሮ፣ የጥበቃና የክትትል ስራውም በሚገባ እንደታሰበበት ስራ አስፈጻሚው ያስረዳሉ። ለዚህም የጥበቃ ካሜራዎችና መከታተያ ቴክኖሎጂዎችን አሟልተናል ይላሉ - አቶ ሲሳይ። የጥበቃ ባለሙያዎች የተሰብሳቢዎችን ትኩረት በማይረብሽ ሁኔታ ስራቸውን ያከናውናሉ።
የኤግዚቢሽንና የጉባኤ አዳራሾች በተጨማሪ፣ ማዕከሉ ሌሎች በርካታ ግንባታዎችንንና አገልግሎቶችን ያካትታል።
ባለ 5 ኮከብ ሆቴል - 980 የእንግዶች ማረፊያ ያለው።
በሆቴል አገልግሎት በከተማችን በትልቅነቱ ቀዳሚነትን የያዘ ሆቴል እንደሚሆን የተናገሩት ከንቲባ አዳነች አበቤ፣ 980 የእንግዳ ማረፊያዎችን መያዝ ይችላል ብለዋል።
እዚህ አካባቢ ምንም ሆቴል አልነበረም ይላሉ - ከንቲባ አዳነች። አሁን ሦስት ሆቴሎች ተሰርተዋል። አራተኛው ከማዶ በኩል አለ። ተደማምረው 1400 የእንግዳ ማረፊያ አገልግሎት የማቅረብ ዓቅም አላቸው።
ምርጥ ምርጥ አፓርትመንቶች በአካባቢው ተሰርተዋል። ለሕዝብ አገልግሎት ክፍት የሚሆኑ አረንጓዴ ስፍራዎችና ተቋማትም ተዘጋጅተዋል።
ፊት ለፊት ለሚ ፓርክ አለ። ሰፊ ነው። ከመስቀል አደባባይ በመቀጠል የሚጠቀስ የከተማችን ትልቅ አደባባይ ነው። ከኤግዚቢሽንና ከጉባኤ ማዕከሉ ጋር ተያይዞ ነው ስራው የሚከናወነው።
ይህ በኢትዮጵያ የመጀመሪያ ግዙፍ እና ዓለም አቀፍ ደረጃውን የጠበቀ “አዲስ ኢንተርናሽናል ኮንቬንሽን ማዕከል”  ትላልቅ አህጉር አቀፍ እና ዓለምአቀፍ ሁነቶችን ለማስተናገድ በሚያስችል ደረጃ ለምረቃ መብቃቱ ለከተማዋ ተጨማሪ ግርማ ሞገስን ያጎናፀፈ ነው፡፡

(የሚጬነ ከናስ አቻ ቦታ እሜስ ዴሬቄነ ኩቶስ አይፌ ዞኡዋ እሜስ) የወላይታ ተረት


ከዕለታት አንድ ቀን አንዲት ደቃቃ ጥንቸል፤ እህል ውሃ ፍለጋ በጫካ ውስጥ ስትዘዋወር፤ አንድ ዝንጀሮ ታገኛታለች፡፡ ጥንቸሏ ግዙፍ ስላልሆነች በየቅጠላ ቅጠሉ ውስጥ እየተሹለከለከች መሄድ እንደምትችል ዝንጀሮ ያውቃል፡፡ ሆኖም አንድ ምክር ሊመክራት ፈልጓል፡፡
“እመት ጥንቸል! የረዥም ጊዜ ወዳጅነታችንን መሰረት በማድረግ ምክር ልለግስሽ እፈልጋለሁ” አላት፡፡
ጥንቸልም፤
“ምን ዓይነት ምክር?” ስትል ጠየቀችው
ዝንጀሮም፤
“ይህን ጫካ አትመኝው፡፡ ሰሞኑን አዳኞች መጥተው ለአውሬ ማጥመጃ የሚሆን ትላልቅ ጉድጓድ ሲቆፍሩ እኔ ዛፍ ላይ ሆኜ አይቻቸዋለሁ፡፡ ስለዚህ ጫካው እንደድሮው ሰላም መስሎሽ ወዲህ ወዲያ አትበይ”
ጥንቸልም፤
“አመሰግናለሁ፡፡ ወጥመዱን የሰሩት ለእኔ አይመስለኝም፡፡ እንደ አንበሳ፣ እንደ ነብር፣ እንደ ዝሆን ላሉት እንጂ እንደኔ ቀጫጫ ለሆነ ፍጡር አይደለም፡፡ ባጋጣሚ ጉድጓድ ውስጥ ብወድቅም መውጫ ብልሃት አላጣም!” ትለዋለች፡፡
ዝንጀሮም፤
“እንግዲህ የወንድምነቴን መክሬሻለሁ፡፡ ብታውቂ እወቂበት” አላትና ሄደ፡፡
ጥንቸል እየተዘዋወረች ቅጠል መበጠሷን ትቀጥላለች፡፡ ጥቂት እንደሄደች ዝንጀሮ እንደፈራው አንድ በቅጠል የተሸፈነ ትልቅ ጉድጓድ ውስጥ ሳታስበው ትወድቃለች፡፡ ጉድጓዱ በጣም ጥልቀት ያለው በመሆኑ በጭራሽ በቀላሉ ልትወጣ የምትችልበት አይደለም፡፡ ስለዚህ አላፊ-አግዳሚውን እንዲያወጣት ለመለመን ተገደደች፡፡
“እባካችሁ አውጡኝ፡፡ እባካችሁ እርዱኝ!” እያለች መጮህ ጀመረች፡፡ ተኩላ ድምጿን ይሰማና ወደ ጉድጓዱ አፍ ይሄዳል፡፡ አጎንብሶም ወደ ጥንቸሏ ያይ ጀመር፡፡
ጥንቸልም፤
“አያ ተኩላ! እባክህ ዘወር በል፡፡ ይሄ ጉድጓድ ለሁለታችን አይበቃንም፡፡ አንተ ያለህበት ቦታ እንደበረሀ የሚያቃጥል አየር ነው ያለው፡፡ እዚህ ግን በጣም ነፋሻና ቅዝቅዝ ያለ አየር ነው ያለው፡፡ ለእኔ በጣም ተስማምቶኛል፡፡ ሆኖም ወደዚህ ለመውረድ ብትችልም እንኳን ቦታው አይበቃንም” አለችው፡፡
ተኩላ፤ የጥንቸሏ ንግግር በጣም አጓጓውና፤ “ልውረድስ ብል በምኔ እወርዳለሁ?” ሲል ጠየቃት፡፡
ጥንቸልም፤
“እዚያ ጉድጓድ አፍ አጠገብ አንድ በገመድ የታሰረ ባሊ አለልህ፡፡ ባሊው ውስጥ ገብተህ በገመዱ ተንሸራተህ መውረድ ትችላለች” አለችው፡፡
ዕውነትም አንድ ባሊ አጠገቡ እንዳለ አየ፡፡ ባሊው ወደ ታች ሲወርድ ጉድጓዱ ውስጥ ያለው ገመድ ጫፍ ወደ ላይ የሚወጣ ነው፡፡ እንደ ፑሊ የሚሰራ ገመድ ነው፡፡ ጉድጓድ ውስጥ ያለውን ጫፍ ጥንቸሏ ይዛለች፡፡
አያ ተኩላ ባሊው ውስጥ ገብቶ ቁልቁል ተምዘግዝጎ ሲወርድ ጥንቸል የገመዱን ጫፍ ይዛ ወደ ላይ ወጣች፡፡
እሱ እየወረደ፣ እሷ እየወጣች መንገድ ላይ ሲተላለፉ፤ ከት ብላ እየሳቀች፤
“አየህ አያ ተኩላ፤ ህይወት ማለት እንደዚህ ናት፡፡ አንዱ ሲወርድ አንዱ ይወጣል!” አለችው፡፡
ተኩላ መሬት ሲደርስ ጥንቸሏ ጉድጓዱ አፋፍ ወጣች!

*   *   *
አንዳንድ ሰዎች አንድ ችግር ውስጥ ሲገቡ ሌላውን እዚያ ውስጥ ነክረው እራሳቸውን ማዳን ይችሉበታል፡፡ ተታልለው እዚያ ችግር ውስጥ የሚገቡት ሞኞች የሚሳሳቱት በአልጠግብ ባይነታቸውና እጉድጓዱ ውስጥ እንኳ ያለው ነገር እንዳያመልጠኝ ብለው ሲስገበገቡ ነው፡፡ የዚህ ዓይነት በርካታ ሰዎች ጉድጓድ ውስጥ ገብተው ቀርተዋል፡፡ ዞሮ ዞሮ ሁለቱም ለሀገርና ለህዝብ አይጠቅሙም፡፡ አደጋን ከሩቅ አይተው የሚያስጠነቅቁ እንደ ዝንጀሮው ያሉ አስተዋዮች ቢኖሩም፣ እህ ብሎ የሚያዳምጣቸው ሰው አያገኙም፡፡ ባንዱ እግር ሌላው እየገባ፣ ህይወት ትቀጥላለች፡፡
ማይ ግሪንፊልድ የተባለ ፀሐፊ፤
“ታሪክ ራሱን ይደግማል፤ ይላል ታሪከኛ ሁሉ
እኔን ያሳሰበኝ ግና፣
ታሪክ በደገመ ቁጥር፣ ዋጋው ይብስ መቀጠሉ” ይላል፡፡ የሚያስከፍለን ዋጋ እየባሰ የሚመጣው እኛ ከታሪክ ለመማር ባለመቻላችን ነው፡፡ የቀደመው የሰራውን ስህተት የኋለኛው ይደግመዋል - ያውም በዚያኛው እየሳቀ፣ እየተሳለቀ! “በእገሌ ጊዜ የተበደላችሁ እጃችሁን አውጡ!” እያለ፡፡ ከንቲባዎች ተቀያይረዋል፡፡ አስተዳዳሪዎች ተቀያይረዋል፡፡ ሚኒስትሮች ተቀያይረዋል ወዘተ… ማንም ከማንም አይማርም፡፡ ሁሌ እኔ ከወደቀው የተሻልኩ ነኝ የሚለውን ለማረጋገጥ የቀደመውን እየረገሙ መቀጠል ነው!! በዚህ ዓይነት ዲሞክራሲያዊ ሥርዓት እመሰርታለሁ ብሎ ማሰብ ቢያንስ የዋህነት ነው፡፡ ከተነሳው ሹም መውሰድ ያለብንን ደግ ነገር ካላወቅን ከዜሮ እንደ መጀመር የከበደ ነው ጉዟችን፡፡
በሁለተኛው የዓለም ጦርነት ወቅት ጀርመኖች ለንደንን በቦምብ በደበደቡ ጊዜ ሦስት ዓይነት ህዝቦች ተፈጥረው ነበር ይባላል፡፡ 1) የተገደሉ 2) ለጥቂት የተሳቱና 3) በርቀት የተሳቱ፡፡ የተገደሉት ሟቾች ናቸውና ስለአደጋው ወሬ አይነዙም፡፡ ለጥቂት የተሳቱት በሰቀቀንና ስቃዩን በማስታወስ የሚኖሩ ሆኑ፡፡ በሩቅ የተሳቱት ግን ቦምብ ጣይ አውሮፕላኖቹን ለመዷቸውና ልበ ሙሉ ሰዎች ሆኑ፤ ይለናል ፀሐፊው ማልኮልም ግላድዌል፡፡ ችግርን መልመድ ደፋርና ልበ - ሙሉ ያደርጋል ነው ነገሩ! ከዚህ ተነስቶ ለአገርና ህዝብ መቆርቆር መቻል መታደል ነው፡፡ በዚህ ወቅት ደሞ ማየት፣ በትክክለኛው ቦታ መገኘትና የሚሰሩትን በቅጡ ማወቅ ግዴታ ነው፡፡ ችግርን ለምዶ መተኛት ግን ሌላ ችግር ነው! ሁሉ በጄ ሁሉ በደጄ እያሉ አግባብነት ያለው ተግባር የማይፈፅሙ አያሌ ናቸው፡፡ የተማሩትና የሰለጠኑበት ሌላ የሚሰሩት ሌላ፤ የሆኑም አያሌ ናቸው! ስለ ግንባታ እያወሩ የማይገነቡ ከአፈረሰ አንድ ናቸው፡፡
መንገድ ሰርቶ በቅጡ ሳንሄድበትና ሳናጣጥመው ከፈረሰ ወይ ሰሪው በቅጡ አላበጀውም፣ ወይ ሂያጆቹ መሄድ አይችሉም፣ አሊያም ሆነ ብለው የሚያጠፉ አሉ ማለት ነው፡፡ ስለዚህ በቅጡ ራስን መመርመር ያስፈልጋል፡፡ “የነቶሎ ቶሎ ቤት ግድግዳው ሰንበሌጥ”ንም ልብ ማለት መልካም ነው፡፡ ሁሉን በውል በውሉ ካላስቀመጥንና ታማኝነትን ብቻ መለኪያ እናድርግ ካልን፣ የተወዛገበ አካሄድ ውስጥ እንሰነቀራለን፡፡ እመጫት እንደ በዛው ፅሁፍ ከዋናው ማረሚያው ይበረክታል፡፡ ከተቃወምንም ዕድሉን ባግባቡ እንጠቀም፡፡
እንዳያማህ ጥራውንም እንተው! በእጃችን ያለውን በወጉ መጠቀም ያስፈልጋል፤ በሁሉም ወገን፡፡ አለበለዚያ “ለማይስቅ ውሻ ነጭ ጥርስ፣ ለማይገላምጥ ዶሮ፣ ቀይ ዐይን ይሰጠዋል” የሚለው የወላይተኛ ተረት ይመጣል፡፡ “ቆሎ ለዘር፤ እንዶድ ለድግር አይሆንም” እንደሚባለው ማለት ነው፡፡    

Saturday, 01 March 2025 21:39

አድዋ፤ ኩራትም ቁጭትም!

ደሳለኝ የኔአካል - ጠበቃና የህግ አማካሪ

 


የአድዋ ድል መልከ ብዙ ነው። ሁሉም ራሱን እያስመሰለ ይስለዋል። ራሱን እያስመሰለ ቢስለው ችግር አይደለም። ምክንያቱም የሁላችንም መልክ አድዋ ላይ አለ። ችግር የሚሆነው አድዋ እኔን ብቻ ይመስላል ካልን ነው። ለምሳሌ በእግዚአብሔር አምሳል ተፈጥረናልና፣ ‘እግዚአብሔርን እመስላለሁ’ ብንል ስህተት አይሆንም። እግዚአብሔርን የምመስለው እኔ ብቻ ነኝ ካልን ግን ስህተትም ኃጢአትም ይሆናል።
እንግዲህ ወሩ የካቲት ነውና፣ ሁላችንንም የሚመስለውን አድዋን እናስታውሳለን። ዛሬ አድዋን የምናስታውሰው ብቻውን አይደለም። የተለመደውንና ስለ አድዋ በጠቀስን ቁጥር ከአፋችን የማንነጥለውን የአዘቦት አረፍተ-ነገራችንን አብረን እናስበዋለን። ይህ አረፍተ ነገራችን “እስከ አፍንጫው የታጠቀውን ስልጡን የጣልያን ሰራዊት በኋላቀር መሳሪያ...” ብሎ የሚጀምር፣ ከድሉ እኩል ዝነኛ የሆነ አረፍተ ነገር ነው። ይህ አረፍተ ነገር ተራ አረፍተ ነገር አይደለም። ጀግንነታችንን ከስንፍናችን አጣምሮ የተሸከመ የማንነታችን መልክ ነው። ራሳችንን ያሞገስንበትና የሰደብንበት የአፋችን ቃል ነው። ለኢትዮጵያውያን (በተለይ ከአክሱም ስልጣኔ ውድቀት በኋላ ለበቀልነው ኢትዮጵያውያን) ፓስፖርትና መታወቂያችን ላይ ከጉርድ ፎቶግራፋችን ይልቅ ይህ አረፍተነገር ቢቀመጥ፣ እኛነታችንን የበለጠ ሊገልፅ ይችላል። ሁሉም መርህ (principle) በስተቀር (exception) አያጣውምና፣ ‘ከአክሱም ውድቀት በኋላ’ ብዬ በአንድ ሀረግ በጠቀለልኩት ሰፊ የዘመን ጥቁር ሰማይ ላይ ሽው እልም ያሉ ተወርዋሪ ኮከቦች መኖራቸው እርግጥ ነው። ይሁን እንጅ ትኩረታችን ከጥቂት ግለሰቦች ግላዊ ጥረትና ስኬት ይልቅ በአጠቃላዩ ማኅበረሰብና ሀገራችን ላይ ስለሆነ መደምደሚያዬን ችኩል ድምዳሜ (hasty generalization) አያደርገውም። መሠረታዊው ጥያቄ፤‘አድዋ እንዴት የኩራትና የቁጭት ምንጭ ሆነ?’ ከፍ ሲል የተጠቀሰው አረፍተ ነገርስ እንዴት የማንነታችን መልክ ሆኖ መጣ? የሚለው ነው።
፩) አድዋ እንደ ኩራት…
የአድዋን ድል ኩራትነት መፃፍ አስቸጋሪ ነገር ነው። እንኳን እኛ የነጭ ዘር ያውቀዋል። አያቶቻችን እስከ አፍንጫው የታጠቀውን ስልጡን ሰራዊት አፍንጫውን ብለው መመለሳቸው እንደ ፀሐይ፡ እንደ ጨረቃ የዓለምን አንድ ገጽ ይዞ ፍንትው ያለ አጠቃላይ እውነት (geberal truth) ነው። በአንድ ግጥሜ ላይ ያልኩትን ደግሜ ብቻ ርዕሱን እዘለዋለሁ።
አድዋ ማለትኮ…
በእናት ሀገር አንገት - የአጥንት አበባ - የደም ጉንጉን ማጥለቅ፣
መስዋዕት እየሆኑ - የነፃነት ጠበል - ላገር መሬት ማፍለቅ።
አድዋ ማለትኮ…
የተግባር መልስ ነው - ለኡምቤርቶ ንቀት - ላንቶኔሊ ስድብ፣
በሞት መሻገር ነው…
የመቀሌን ምሽግ - ያምባላጌን ጉድብ፤
በባርነት ገደል በግዞት ሸለቆ…
ክቡር ደም ነስንሶ - አጥንት ጎዝጉዞ
ባህርን ሰንጥቆ - ሞቶ ማሻገር ነው - ያገርን እጅ ይዞ።
(ተይው ፖለቲን ዝም ብለሽ
ሳሚኝ - 2014 ዓ.ም)

፪) አድዋ እንደ ቁጭት…
“እስከ አፍንጫው የታጠቀውን ስልጡን የጣልያን ሰራዊት በኋላቀር መሳሪያ...” የሚለው ወዝ ጠገብ (እና ጆሮ ጠገብ) አረፍተ-ነገር በአንድ በኩል ስልጡን የኢጣልያ ሰራዊት፣ በሌላ በኩል ኋላቀር የኢትዮጵያ ሰራዊት ግንባር ለግንባር የተፋጠጡበት አረፍተ ነገር ነው።
እንደሚታወቀው ኢትዮጵያችን የሦስት ሺህ ዓመት (አምስት ሺህ የሚያደርጉትም አሉ) የመንግሥትነት ታሪክ ያላት፣ ዓለም ከመንቃቱ በፊት በሰማይ በራሪ በምድር ተሽከርካሪ የፈለሰፈች (በራሪ ሰዎችም የነበሯት)፣ ባህር ተሻግራ፣ ዱር መንጥራ በዚህ እስከ ምስርና የመን፣ በዚያ እስከ ማዳጋስካር የገዛች፣ ሱዳንን አስገብራ ወርቅ የምታፍስ (ሰርዶ አልግጥም አለ የፋሲል ፈረሱ፣
ክምር የሱዳን ወርቅ ገፈራው ነው ለእሱ፤ የሚለው ሕዝባዊ ግጥም ለዚህ ምስክር ነው)፣ የአትላንቲክ ውቅያኖስ ደቡባዊ ግማሽ ኢትዮጵያ ውቅያኖስ ተብሎ ለስሟ ክብር የተሰየመላት (ለሙሽርነቷ ስም ሲወጣላት ዳቦ ሳይሆን ውቅያኖስ የተቆረሰላት ሀገር ናት ልንል እንችላለን)፣ ከሮማ ግዛተ-አጼ (Roman empire) ጋር የሚገዳደርና ትከሻ ለትከሻ የሚገፋፋ የአክሱም ስልጣኔ የሚባል ግዙፍ ስልጣኔ የነበራት፣ የመስቀል ጦረኞች (Crusaders) ቄስ ንጉሥ ዮሐንስ (Prester John) የሚባል ንጉሥ መጥቶ ያድነናል የዚያ ንጉሥ ሀገርም ኢትዮጵያ ነች ብለው ተስፋ ያደረጉባት፣ የተስፋቸው ምድር (ከተስፋቸውም ከኢትዮጵያ የተነሳ እንዲል ታላቁ መፅሐፍ) ነበረች። ከአክሱም ውድቀት በኋላ አንዱ በአንዱ ላይ እየተነባበረ እንደ ህልም ሩጫ እያንሸራተተ ሲደፍቃት በኖረው ተከታታይና ተቀጣጣይ ጦርነት ምክንያት ስትወድቅ ስትነሳ ኖረች። የጎንደሩ ማዕከላዊ መንግሥት እየፈዘዘ መምጣቱን ተከትሎም፣ በስሁል ሚካኤል እግር የገባው ዘመነ መሳፍንት ከትልቁ ራስ አሊ እስከ ትንሹ ራስ አሊ ድረስ ለሰባ አመታት ያህል ሀገሪቱን በመሳፍንቱ ኮቴ ስር ሲያስደከድካት ቆዬ። በኋላም የቋራው ካሳ ራዕዩን ስሎ ጦሩን ወልውሎ መጣ። መሳፍንቱ በጦርና በቁማር (Conspiracy) የተካፈሏትን ሀገር፣ ከየእጃቸው ነጥቆ አንድ ላይ ሰበሰባት። ይህ የሆነው እ.ኤ.አ በ1855 (1848 ዓ.ም) ነው።
ኢጣልያ በሌላ አንፃር ከስመ ገናናው የሮማ ግዛተ አጼ (Roman Empire) መፈራረስ በኋላ አንድነት ያልነበራት፣ የናፖሊዮኗ ፈረንሳይ ፍዳዋን የምታበላት በኋላም፣ ኦስትሪያ የተፅዕኖ መዳፏን ትከሻዋ ላይ የጫነችባት፣ ጳጳሳትና ፊውዳል መሳፍንት እንደ ጉሊት ሸቀጥ በመደብ በመደብ ከፍለው የሚሸጧቸው የሚለውጧቸው ግዛቶችና የከተማ መንግስታት መደብር ነበረች። እ.ኤ.አ ከ1830ዎቹ ጀምሮ ያቆጠቆጠውና በዋናነትም በአብዮተኛው ጉሴፔ ጋሪባልዲና በቀይ ለባሽ ጦሩ የተመራው የውህደት እንቅስቃሴ ተጀምሮ በፔድሞንቱ ንጉሥ ዳግማዊ ቪክቶር ኢማኑኤል ንግሥና ተጠናቀቀ። ጣልያኖች Risorgimento (እንደገና መነሳት) ብለው የሚጠሩት የውህደት ንቅናቄ እ.ኤ.አ በ1861 ተጠናቋል የሚሉ ቢኖሩም፣ የጳጳሱ መዲና የነበረችውን ሮምን የመላው ኢጣልያ ዋና ከተማው አድርጎ የተጠናቀቀው ግን እ.ኤ.አ በ1871 ነው። በብዙ ፍላጎቶች መፋተር ወዲያና ወዲህ ተወጥሮ የነበረው የውህደት መንገድ፣ የኢጣልያ ውህደት እ.ኤ.አ በ1871 ተጠናቀቀ።
1861ን እንኳን ብንይዝ ኢትዮጵያ ሀገራችን ከመሳፍንቱ የፍዳ ዘመን ከተላቀቀችና ካሳም ዳግማዊ ቴዎድሮስ ተብሎ ከነገሠ (እ.ኤ.አ 1855) ከስድስት ዓመት በኋላ መሆኑ ነው። የሁለቱንም ሀገራት ውህደት መጠናቀቂያ እንያዝ ካልንም እንጦጦ በኢትዮጵያ አቆጣጠር በ1871 ዓ.ም ዋና ከተማ የነበረች በመሆኑ አነሰም በዛም ተቀራራቢ ጊዜ ላይ ውህደት የጨረሱ ሀገራት መሆናቸውን ታሪክ ያስረዳል።
እንግዲህ ጣልያኖች ከእኛ በፊት ወድቀው… ከእኛ በኋላ ተነስተው… እ.ኤ.አ በ1896 (ውህደታቸውን ጨርሰው ሀገር ከሆኑ ከ25 ዓመት በኋላ) ባህር ተሻግሮ ሀገራትን ማብረክረክ የቻለ እስከ አፍንጫው የታጠቀ ዘመናዊ ሰራዊት እና ክንደ ብርቱ ሀገር ገነቡ። በዚያ ፍጥነት አፍሪካ ተሻግረው እግራቸውን በቀይ ባህር ውሃ ታጠቡ። እኛ ከእነሱ በኋላ ወድቀን… ከእነሱ ቀድመን ተነስተን… እ.ኤ.አ በ1896 (1888 ዓ.ም) (ዘመነ መሳፍንትን ካጠፋን ከ41 ዓመት በኋላ) አድዋ ላይ ምን ይዘን ተሰለፍን? ብለን ስንጠይቅ ጋሻ፣ ጦር፣ በጣም ጥቂት ‘ቁመህ ጠብቀኝ’ ጠበንጃዎች (እነ ወጨፎ) እና በባዶ እጅም ቢሆን የሚተናነቁ ጀግና ተዋጊዎችን። በጀግኖቻችን ሞት አይፈሬነት ምክንያት አሸነፍን። በ41 ዓመቱ ጉዞ ምን ገነባን ስንል ግን መልሱ ነፍስ የሚያሸማቅቅ ሆኖ ብቅ ይላል። እነሱ እንዴት ሰለጠኑ? እንዴት ኋላ ቀረን? ትንሳኤያችን ከትንሳኤያቸው ስድስት ዓመት ቀድሞ እያለ እንዴት ቆመን አሳለፍናቸው? ከእኛ በኋላ ተወልደው ምን ቢንቁን አጥራችንን ነቀነቁ? አያያዛችን እንዴት ሆኖ ቢታያቸው ስንቃችንን ለመቀማት ተራኮቱ? ከአድዋ በኋላም ሳንነቃ ቀረን። የዳግማዊ ምኒልክን ሽፍን ጫማ መልበስ ስናሽሟጥጥ፣ ከውጭ ያስመጣነውን መኪና እንኳ መልመድ አቅቶን የሰይጣን ፈረስ እያልን በየግብር አዳራሹ አፍ ገጥመን ስናንሾካሹክ፣ የድንጋይ ወፎጯችንን መጅ ወርውረን ወደ ዘመን አመጣሹ ወፍጮ ለመራመድ እንደ እግረ-ተከል ህፃን ስንከነበል ጣልያን ግን ከአርባ ዓመት በኋላ አውሮፕላንና መድፍ ሰርታ ድጋሜ መጣችብን። እነሱ ስልጡን እኛ ኋላቀር የሚለውን ሀረግ ክፉኛ ከመላመዳችን የተነሳ ስንናገረውም የምንኮራበት ይመስለኛል።
ዶጋሊ ላይ እነሱ ስልጡን እኛ ኋላ ቀር
አድዋ ላይ እነሱ ስልጡን እኛ ኋላ ቀር
ማይጨው ላይ እነሱ ስልጡን እኛ ኋላ ቀር
ካራማራ ላይ ሶማሌ ስልጡን እኛ ኋላ ቀር
መቼ ይሆን ግልባጩን ታሪክ ሰርተን ‘እኛ ስልጡን እነሱ ኋላቀር’ የሚል ትርክት ገልብጠን የምንፅፈው? መቼ ይሆን ሀገራችን እኩል ለእኩል፣ ስልጣኔ ለስልጣኔ፣ ቴክኖሎጅ ለቴክኖሎጂ የምትገዳደረው? መቼ ይሆን ከጦር ሜዳ መልስም ሀገር እንዳለችን የምንረዳው? መቼ?

Saturday, 01 March 2025 21:39

አድዋ፤ ኩራትም ቁጭትም!

ደሳለኝ የኔአካል - ጠበቃና የህግ አማካሪ

 


የአድዋ ድል መልከ ብዙ ነው። ሁሉም ራሱን እያስመሰለ ይስለዋል። ራሱን እያስመሰለ ቢስለው ችግር አይደለም። ምክንያቱም የሁላችንም መልክ አድዋ ላይ አለ። ችግር የሚሆነው አድዋ እኔን ብቻ ይመስላል ካልን ነው። ለምሳሌ በእግዚአብሔር አምሳል ተፈጥረናልና፣ ‘እግዚአብሔርን እመስላለሁ’ ብንል ስህተት አይሆንም። እግዚአብሔርን የምመስለው እኔ ብቻ ነኝ ካልን ግን ስህተትም ኃጢአትም ይሆናል።
እንግዲህ ወሩ የካቲት ነውና፣ ሁላችንንም የሚመስለውን አድዋን እናስታውሳለን። ዛሬ አድዋን የምናስታውሰው ብቻውን አይደለም። የተለመደውንና ስለ አድዋ በጠቀስን ቁጥር ከአፋችን የማንነጥለውን የአዘቦት አረፍተ-ነገራችንን አብረን እናስበዋለን። ይህ አረፍተ ነገራችን “እስከ አፍንጫው የታጠቀውን ስልጡን የጣልያን ሰራዊት በኋላቀር መሳሪያ...” ብሎ የሚጀምር፣ ከድሉ እኩል ዝነኛ የሆነ አረፍተ ነገር ነው። ይህ አረፍተ ነገር ተራ አረፍተ ነገር አይደለም። ጀግንነታችንን ከስንፍናችን አጣምሮ የተሸከመ የማንነታችን መልክ ነው። ራሳችንን ያሞገስንበትና የሰደብንበት የአፋችን ቃል ነው። ለኢትዮጵያውያን (በተለይ ከአክሱም ስልጣኔ ውድቀት በኋላ ለበቀልነው ኢትዮጵያውያን) ፓስፖርትና መታወቂያችን ላይ ከጉርድ ፎቶግራፋችን ይልቅ ይህ አረፍተነገር ቢቀመጥ፣ እኛነታችንን የበለጠ ሊገልፅ ይችላል። ሁሉም መርህ (principle) በስተቀር (exception) አያጣውምና፣ ‘ከአክሱም ውድቀት በኋላ’ ብዬ በአንድ ሀረግ በጠቀለልኩት ሰፊ የዘመን ጥቁር ሰማይ ላይ ሽው እልም ያሉ ተወርዋሪ ኮከቦች መኖራቸው እርግጥ ነው። ይሁን እንጅ ትኩረታችን ከጥቂት ግለሰቦች ግላዊ ጥረትና ስኬት ይልቅ በአጠቃላዩ ማኅበረሰብና ሀገራችን ላይ ስለሆነ መደምደሚያዬን ችኩል ድምዳሜ (hasty generalization) አያደርገውም። መሠረታዊው ጥያቄ፤‘አድዋ እንዴት የኩራትና የቁጭት ምንጭ ሆነ?’ ከፍ ሲል የተጠቀሰው አረፍተ ነገርስ እንዴት የማንነታችን መልክ ሆኖ መጣ? የሚለው ነው።
፩) አድዋ እንደ ኩራት…
የአድዋን ድል ኩራትነት መፃፍ አስቸጋሪ ነገር ነው። እንኳን እኛ የነጭ ዘር ያውቀዋል። አያቶቻችን እስከ አፍንጫው የታጠቀውን ስልጡን ሰራዊት አፍንጫውን ብለው መመለሳቸው እንደ ፀሐይ፡ እንደ ጨረቃ የዓለምን አንድ ገጽ ይዞ ፍንትው ያለ አጠቃላይ እውነት (geberal truth) ነው። በአንድ ግጥሜ ላይ ያልኩትን ደግሜ ብቻ ርዕሱን እዘለዋለሁ።
አድዋ ማለትኮ…
በእናት ሀገር አንገት - የአጥንት አበባ - የደም ጉንጉን ማጥለቅ፣
መስዋዕት እየሆኑ - የነፃነት ጠበል - ላገር መሬት ማፍለቅ።
አድዋ ማለትኮ…
የተግባር መልስ ነው - ለኡምቤርቶ ንቀት - ላንቶኔሊ ስድብ፣
በሞት መሻገር ነው…
የመቀሌን ምሽግ - ያምባላጌን ጉድብ፤
በባርነት ገደል በግዞት ሸለቆ…
ክቡር ደም ነስንሶ - አጥንት ጎዝጉዞ
ባህርን ሰንጥቆ - ሞቶ ማሻገር ነው - ያገርን እጅ ይዞ።
(ተይው ፖለቲን ዝም ብለሽ
ሳሚኝ - 2014 ዓ.ም)

፪) አድዋ እንደ ቁጭት…
“እስከ አፍንጫው የታጠቀውን ስልጡን የጣልያን ሰራዊት በኋላቀር መሳሪያ...” የሚለው ወዝ ጠገብ (እና ጆሮ ጠገብ) አረፍተ-ነገር በአንድ በኩል ስልጡን የኢጣልያ ሰራዊት፣ በሌላ በኩል ኋላቀር የኢትዮጵያ ሰራዊት ግንባር ለግንባር የተፋጠጡበት አረፍተ ነገር ነው።
እንደሚታወቀው ኢትዮጵያችን የሦስት ሺህ ዓመት (አምስት ሺህ የሚያደርጉትም አሉ) የመንግሥትነት ታሪክ ያላት፣ ዓለም ከመንቃቱ በፊት በሰማይ በራሪ በምድር ተሽከርካሪ የፈለሰፈች (በራሪ ሰዎችም የነበሯት)፣ ባህር ተሻግራ፣ ዱር መንጥራ በዚህ እስከ ምስርና የመን፣ በዚያ እስከ ማዳጋስካር የገዛች፣ ሱዳንን አስገብራ ወርቅ የምታፍስ (ሰርዶ አልግጥም አለ የፋሲል ፈረሱ፣
ክምር የሱዳን ወርቅ ገፈራው ነው ለእሱ፤ የሚለው ሕዝባዊ ግጥም ለዚህ ምስክር ነው)፣ የአትላንቲክ ውቅያኖስ ደቡባዊ ግማሽ ኢትዮጵያ ውቅያኖስ ተብሎ ለስሟ ክብር የተሰየመላት (ለሙሽርነቷ ስም ሲወጣላት ዳቦ ሳይሆን ውቅያኖስ የተቆረሰላት ሀገር ናት ልንል እንችላለን)፣ ከሮማ ግዛተ-አጼ (Roman empire) ጋር የሚገዳደርና ትከሻ ለትከሻ የሚገፋፋ የአክሱም ስልጣኔ የሚባል ግዙፍ ስልጣኔ የነበራት፣ የመስቀል ጦረኞች (Crusaders) ቄስ ንጉሥ ዮሐንስ (Prester John) የሚባል ንጉሥ መጥቶ ያድነናል የዚያ ንጉሥ ሀገርም ኢትዮጵያ ነች ብለው ተስፋ ያደረጉባት፣ የተስፋቸው ምድር (ከተስፋቸውም ከኢትዮጵያ የተነሳ እንዲል ታላቁ መፅሐፍ) ነበረች። ከአክሱም ውድቀት በኋላ አንዱ በአንዱ ላይ እየተነባበረ እንደ ህልም ሩጫ እያንሸራተተ ሲደፍቃት በኖረው ተከታታይና ተቀጣጣይ ጦርነት ምክንያት ስትወድቅ ስትነሳ ኖረች። የጎንደሩ ማዕከላዊ መንግሥት እየፈዘዘ መምጣቱን ተከትሎም፣ በስሁል ሚካኤል እግር የገባው ዘመነ መሳፍንት ከትልቁ ራስ አሊ እስከ ትንሹ ራስ አሊ ድረስ ለሰባ አመታት ያህል ሀገሪቱን በመሳፍንቱ ኮቴ ስር ሲያስደከድካት ቆዬ። በኋላም የቋራው ካሳ ራዕዩን ስሎ ጦሩን ወልውሎ መጣ። መሳፍንቱ በጦርና በቁማር (Conspiracy) የተካፈሏትን ሀገር፣ ከየእጃቸው ነጥቆ አንድ ላይ ሰበሰባት። ይህ የሆነው እ.ኤ.አ በ1855 (1848 ዓ.ም) ነው።
ኢጣልያ በሌላ አንፃር ከስመ ገናናው የሮማ ግዛተ አጼ (Roman Empire) መፈራረስ በኋላ አንድነት ያልነበራት፣ የናፖሊዮኗ ፈረንሳይ ፍዳዋን የምታበላት በኋላም፣ ኦስትሪያ የተፅዕኖ መዳፏን ትከሻዋ ላይ የጫነችባት፣ ጳጳሳትና ፊውዳል መሳፍንት እንደ ጉሊት ሸቀጥ በመደብ በመደብ ከፍለው የሚሸጧቸው የሚለውጧቸው ግዛቶችና የከተማ መንግስታት መደብር ነበረች። እ.ኤ.አ ከ1830ዎቹ ጀምሮ ያቆጠቆጠውና በዋናነትም በአብዮተኛው ጉሴፔ ጋሪባልዲና በቀይ ለባሽ ጦሩ የተመራው የውህደት እንቅስቃሴ ተጀምሮ በፔድሞንቱ ንጉሥ ዳግማዊ ቪክቶር ኢማኑኤል ንግሥና ተጠናቀቀ። ጣልያኖች Risorgimento (እንደገና መነሳት) ብለው የሚጠሩት የውህደት ንቅናቄ እ.ኤ.አ በ1861 ተጠናቋል የሚሉ ቢኖሩም፣ የጳጳሱ መዲና የነበረችውን ሮምን የመላው ኢጣልያ ዋና ከተማው አድርጎ የተጠናቀቀው ግን እ.ኤ.አ በ1871 ነው። በብዙ ፍላጎቶች መፋተር ወዲያና ወዲህ ተወጥሮ የነበረው የውህደት መንገድ፣ የኢጣልያ ውህደት እ.ኤ.አ በ1871 ተጠናቀቀ።
1861ን እንኳን ብንይዝ ኢትዮጵያ ሀገራችን ከመሳፍንቱ የፍዳ ዘመን ከተላቀቀችና ካሳም ዳግማዊ ቴዎድሮስ ተብሎ ከነገሠ (እ.ኤ.አ 1855) ከስድስት ዓመት በኋላ መሆኑ ነው። የሁለቱንም ሀገራት ውህደት መጠናቀቂያ እንያዝ ካልንም እንጦጦ በኢትዮጵያ አቆጣጠር በ1871 ዓ.ም ዋና ከተማ የነበረች በመሆኑ አነሰም በዛም ተቀራራቢ ጊዜ ላይ ውህደት የጨረሱ ሀገራት መሆናቸውን ታሪክ ያስረዳል።
እንግዲህ ጣልያኖች ከእኛ በፊት ወድቀው… ከእኛ በኋላ ተነስተው… እ.ኤ.አ በ1896 (ውህደታቸውን ጨርሰው ሀገር ከሆኑ ከ25 ዓመት በኋላ) ባህር ተሻግሮ ሀገራትን ማብረክረክ የቻለ እስከ አፍንጫው የታጠቀ ዘመናዊ ሰራዊት እና ክንደ ብርቱ ሀገር ገነቡ። በዚያ ፍጥነት አፍሪካ ተሻግረው እግራቸውን በቀይ ባህር ውሃ ታጠቡ። እኛ ከእነሱ በኋላ ወድቀን… ከእነሱ ቀድመን ተነስተን… እ.ኤ.አ በ1896 (1888 ዓ.ም) (ዘመነ መሳፍንትን ካጠፋን ከ41 ዓመት በኋላ) አድዋ ላይ ምን ይዘን ተሰለፍን? ብለን ስንጠይቅ ጋሻ፣ ጦር፣ በጣም ጥቂት ‘ቁመህ ጠብቀኝ’ ጠበንጃዎች (እነ ወጨፎ) እና በባዶ እጅም ቢሆን የሚተናነቁ ጀግና ተዋጊዎችን። በጀግኖቻችን ሞት አይፈሬነት ምክንያት አሸነፍን። በ41 ዓመቱ ጉዞ ምን ገነባን ስንል ግን መልሱ ነፍስ የሚያሸማቅቅ ሆኖ ብቅ ይላል። እነሱ እንዴት ሰለጠኑ? እንዴት ኋላ ቀረን? ትንሳኤያችን ከትንሳኤያቸው ስድስት ዓመት ቀድሞ እያለ እንዴት ቆመን አሳለፍናቸው? ከእኛ በኋላ ተወልደው ምን ቢንቁን አጥራችንን ነቀነቁ? አያያዛችን እንዴት ሆኖ ቢታያቸው ስንቃችንን ለመቀማት ተራኮቱ? ከአድዋ በኋላም ሳንነቃ ቀረን። የዳግማዊ ምኒልክን ሽፍን ጫማ መልበስ ስናሽሟጥጥ፣ ከውጭ ያስመጣነውን መኪና እንኳ መልመድ አቅቶን የሰይጣን ፈረስ እያልን በየግብር አዳራሹ አፍ ገጥመን ስናንሾካሹክ፣ የድንጋይ ወፎጯችንን መጅ ወርውረን ወደ ዘመን አመጣሹ ወፍጮ ለመራመድ እንደ እግረ-ተከል ህፃን ስንከነበል ጣልያን ግን ከአርባ ዓመት በኋላ አውሮፕላንና መድፍ ሰርታ ድጋሜ መጣችብን። እነሱ ስልጡን እኛ ኋላቀር የሚለውን ሀረግ ክፉኛ ከመላመዳችን የተነሳ ስንናገረውም የምንኮራበት ይመስለኛል።
ዶጋሊ ላይ እነሱ ስልጡን እኛ ኋላ ቀር
አድዋ ላይ እነሱ ስልጡን እኛ ኋላ ቀር
ማይጨው ላይ እነሱ ስልጡን እኛ ኋላ ቀር
ካራማራ ላይ ሶማሌ ስልጡን እኛ ኋላ ቀር
መቼ ይሆን ግልባጩን ታሪክ ሰርተን ‘እኛ ስልጡን እነሱ ኋላቀር’ የሚል ትርክት ገልብጠን የምንፅፈው? መቼ ይሆን ሀገራችን እኩል ለእኩል፣ ስልጣኔ ለስልጣኔ፣ ቴክኖሎጅ ለቴክኖሎጂ የምትገዳደረው? መቼ ይሆን ከጦር ሜዳ መልስም ሀገር እንዳለችን የምንረዳው? መቼ?

የኢትዮጵያና ኤርትራ መንግሥታት ወደ ጦርነት ከሚያስገቡ ጠብ አጫሪ ድርጊቶች መቆጠብ እንዳለባቸው የተጠቆመ ሲሆን፤ ለሁለቱም አገራት የተሻለ ቀረቤታ ያላቸው ወገኖች የእርቅ ጥረት ማድረግ አለባቸው ተብሏል፡፡
ከሰሞኑ በኢትዮጵያና ኤርትራ መንግሥታት መካከል የተፈጠረው የቃላት ጦርነት የብዙዎችን ትኩረት የሳበ ሲሆን፤ አገራቱ ወደ ጦርነት እንዳይንደረደሩ በርካቶች ስጋታቸውን ገልጸዋል። የአፍሪካ ቀንድ ጉዳዮች ተመራማሪና የዓለም አቀፍ ግንኙነቶች ምሁር አቶ ኢያሱ ሃይለሚካኤል ለአዲስ አድማስ በሰጡት አስተያየት፤ በኢትዮጵያና ኤርትራ መካከል ለረዥም ጊዜ የቆየ ፍትጊያ እንደነበረና አሁን የሚስተዋለው የቃላት ግጭት ከፖለቲካዊና መልክዓምድራዊ ጉዳዮች ጋር እንደሚገናኝ ይገልጻሉ፡፡
“የሁለቱ አገራት ፍትጊያ በበርካታ ታሪካዊ አጋጣሚዎች ውስጥና በተለዋዋጭ ሁኔታዎች መካከል የዘለቀ ነው” የሚሉት አቶ ኢያሱ፤ በተለይም ኤርትራ ነጻነቷን ካወጀችበት ጊዜ በኋላ የተፈጠሩ አለመግባባቶች በሰፊው መስተዋላቸውን ያስታውሳሉ፡፡ አክለውም፤ በቀድሞው የኢሕአዴግ መንግስትና በኤርትራ መንግስት መካከል የኢኮኖሚ ፖሊሲ አቅጣጫ ልዩነቶች እንደነበሩ ጠቁመዋል፡፡
ለአብነት ያህል፣ ግንቦት 4 ቀን 1990 ዓ.ም. የተቀሰቀሰው የኢትዮ-ኤርትራ ጦርነት ከድንበር ይልቅ የኢኮኖሚ ጉዳይ መነሻ ምክንያት እንደነበር እኚሁ ምሁር አስረድተዋል። ጦርነቱ በአልጀርስ ስምምነት ከተቋጨ በኋላ የዘለቀው ጦርነትም ሆነ ሰላም የሌለበት ሁኔታ፣ በመጋቢት ወር 2010 ዓ.ም. ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ ወደ ስልጣን ከመጡ በኋላ የሁለቱ አገራት ግንኙነት እንደታደሰ ጠቅሰዋል።
በኢጣልያ ለረዥም ዓመታት በኤርትራ የተተከለው የቅኝ ግዛትና ዓለም አቀፉ የፖለቲካ ሁኔታ ያስከተለው ተጽዕኖ ኢትዮጵያና ኤርትራን ሲያጋጭ መቆየቱን ያወሱት አቶ ኢያሱ፤ ጥቅምት 24 ቀን 2013 ዓ.ም. ተቀስቅሶ ለሁለት ዓመታት ሲካሄድ የከረመው የሰሜን ኢትዮጵያው ጦርነት በፕሪቶሪያ ዘላቂ የግጭት ማቆም ስምምነት ሲቋጭ፣ ከኢትዮጵያ መንግስት አዳዲስ ጥያቄዎች እንደቀረቡ አመልክተዋል። ከእነዚህም ጥያቄዎች ውስጥ የባሕር በር የማግኘት ጥያቄ አንዱ እንደሆነ በማንሳት፣ ይህንን ጥያቄ ለማሳካት የኢትዮጵያ መንግስት አጥቂ (offensive) የውጭ ጉዳይ ፖሊሲ መከተሉን አስረድተዋል።
አቶ ኢያሱ “የባሕር በር ጥያቄ ከኢትዮጵያ ኢኮኖሚ ጋር እያደገ የሚመጣ ጥያቄ ነው። ይኸው ጥያቄ ግጭትና ጦርነትን ሊፈጥር ይችላል። በእነዚሁ ሁኔታዎች የሚፈጠረው ጉዳት ከፍተኛ ይሆናል” በማለት ማብራሪያቸውን ቀጥለው፣ የኢትዮጵያ የባሕር በር ጥያቄ በአፍሪካ ቀንድ ቀጣና ላይ ውጥረትን እንደፈጠረ ተናግረዋል። ከቅርብ ጊዜያት ወዲህ የሚስተዋሉ በሁለቱ አገራት የሚሰነዘሩ የቃላት ምልልሶች፣ በአገራቱ መካከል የተፈጠረው የዲፕሎማሲ ግንኙነት መቀዛቀዝ ምልክት መሆናቸውን አያይዘው ገልጸዋል።
“የሰሜን ኢትዮጵያው ጦርነት መርገብ በኢትዮጵያና ኤርትራ መካከል ያለውን ግንኙነት እያሻከረው መጥቷል” ያሉት ምሁሩ፤ “ሁለቱም አገራት ወደ ጦርነት የሚሄዱበት ጊዜ አጭር ባይሆንም፣ የተወሰኑ የእርስ በርስ ትንኮሳዎች ሊኖር እንደሚችሉ ግምታቸውን ሰጥተዋል።
“እንደ አገር ከአሁኑ መፍትሔ መፈለግ ያስፈልጋል። የቀይ ባሕር ጉዳይ ቀላል አይደለም። ምክንያቱም ዓለም አቀፍ ፍላጎቶች ያሉበት አካባቢ ነው” ያሉት አቶ ኢያሱ፤ ጦርነቱ ከተጀመረ የውጭ ሃይሎች ተጽዕኖ ሊታከልበት እንደሚችል ጠቅሰዋል። “የሁለቱ አገራት ዲፕሎማሲያዊ ውጥረት ወደ ጡዘት ደረጃ ደርሷል። ከዚህም ባሻገር፣ የውክልና ጦርነት ሊኖር ይችላል። ነገር ግን ኤርትራ ይህንን ጦርነት ለማድረግ የኢኮኖሚ አቅም ‘አላት ወይ?’ የሚለው ጉዳይ አጠያያቂ ነው” ብለዋል።
ከዚህ የጦርነት ስጋት ለመውጣት “መፍትሔው ምንድን ነው?” የሚል ጥያቄ ከአዲስ አድማስ የቀረበላቸው አቶ ኢያሱ በሰጡት ምላሽ፣ ለኢትዮጵያም ሆነ ለኤርትራ ቀረቤታ ያላቸው መንግስታት፣ ተቋማትና ቡድኖች የእርቅ እንቅስቃሴ የሚጀምሩበት መንገድ ቢፈጠር፣ መልካም መሆኑን ጠቁመው፤ በምሳሌነት ሩሲያ፣ ቻይና እና እንደ ኢጣልያ ያሉ የአውሮጳ አገራት፣ ብሎም የተባበሩት አረብ ኤሜሬቶችና ሳዑዲ አረቢያ ይህንን የእርቅ እንቅስቃሴ “መጀመር ይኖርባቸዋል” ብለዋል፡፡
በተጨማሪም፣ በሁለቱም አገራት በኩል ከጠብ አጫሪ ድርጊቶች መቆጠብ እንደሚያስፈልግ ያሳሰቡት አቶ ኢያሱ፤ “ከብሔራዊ ጥቅም አንጻር በኢትዮጵያ በኩል ጥንቃቄ ማድረግ ያስፈልጋል” ሲሉ አስረድተዋል።
ከሁሉም በላይ የሁለቱ አገራት ዲፕሎማሲያዊ ግንኙነት በጥንቃቄ መያዝ ያለበት መሆኑን አጽንዖት ሰጥተዋል።

ተቃዋሚ ፓርቲዎች በአማራ ክልል፣ ምስራቅ ጎጃም ዞን፣ ጎንቻ ሲሶ እነሴ ወረዳ፣ “አነገሽ” በተባለ ቀበሌ፣ ልዩ ስሙ “ሐሙስ ገበያ” በተባለ ስፍራ “ተፈጽሟል” ያሉትን የድሮን ጥቃት አውግዘዋል። ፓርቲዎቹ ጥቃቱን “የጦር ወንጀል” ሲሉ ጠርተውታል።
እናት ፓርቲ፣ መኢአድ፣ ኢሕአፓ እና አማራ ግዮናዊ ንቅናቄ በጋራ፣ ሐሙስ የካቲት 20 ቀን 2017 ዓ.ም. ባወጡት መግለጫ፣ በዚሁ የድሮን ጥቃት ታዳጊ ህጻናትን ጨምሮ 16 ንጹሃን ሰዎች እንደተገደሉና ሌሎች 11 ሰዎች ክፉኛ እንደቆሰሉ አስታውቀዋል። ኢትዮጵያ የፈረመቻቸው እንደጄኔቫ እና ዘኼግ ያሉ ስምምነቶች፣ እንዲሁም መሰል ዓለም አቀፍ ሕጎች ላይ እንደሰፈረው በጦርነት ወቅት ንጹሃን መጠበቅ እንዳለባቸው፣ የሕዝብ መገልገያ ተቋማትም የጦር ዒላማ መኾን እንደሌለባቸው ቢደነገግም፣ “መንግስት ግን መሰል ድንጋጌዎችንና አገር እየተመራችበት ያለውን ሕገ መንግስት ጭምር በጣሰና ሃላፊነት በጎደለው አኳኋን እንዲመራቸው ጭምር የመረጡትን ንጹሃን ዜጎችን፣ የጤና ተቋማትን፣ ትምሕርት ቤቶችን፣ የዕምነት ቦታዎችን የጥቃት ዒላማ ካደረገ ውሎ አድሯል” በማለት እነዚሁ ፓርቲዎች ነቅፈዋል።
ፓርቲዎቹ መግለጫቸውን ሲቀጥሉ፣ መንግስት ፖለቲካዊ ድክመቱን ለመሸፈን “የጸጥታ ሃይሉን ወደ ፖለቲካው በመሳብና እንዲህ ያሉ በጦር ወንጀል ጭምር የሚያስጠይቁ የንጹሃን ጭፍጨፋ፣ መሰወርና የዘፈቀደ ግድያዎችን እንዲፈጽም የእጅ ጥምዘዛ ያህል እያስገደደውና እያሳሳተው ይገኛል” በማለት ከስሰዋል።
አክለውም፣ “መንግስት ከጊዜ ወደጊዜ እየሰከነና ቀልብ እየገዛ ከዚህ ዓይነት ሃላፊነት የጎደለው ተግባሩ ‘ይታቀባል’ ሲባል፣ የጥቃት አድማሱን እያሰፋ፣ ከመጸጸት ይልቅ በዕኩይ ድርጊቱ ይበልጥ እየተኩራራ፣ ለዕድገት ይውል የነበረን ከፍተኛ የአገር ሃብት ሰበብ እየፈለገ ለንፁሃን ጥቃት እያዋለው ይገኛል” ሲሉ ፓርቲዎቹ አመልክተዋል።
ጥቃቱን “መንግስታዊ ሽብር” እና “የጦር ወንጀል” ሲሉ የጠሩት ፓርቲዎቹ፣ ዓለምአቀፉ ማሕበረሰብ፣ የፖለቲካ ልሂቃን፣ የሃይማኖት አባቶች፣ ምሁራን፣ የመገናኛ ብዙሃንና የሰብዓዊ መብት ተማጋቾች እንዲቃወሙት ጠይቀዋል። አያይዘውም፣ ፓርቲዎቹ ትግላቸውን አጠናክረው እንደሚቀጥሉ ገልጸዋል።
በሌላ በኩል፣ እናት ፓርቲ በኦሮሚያ ክልል፣ ጅማ ዞን፣ ጌራ ወረዳ ከየካቲት 6 ቀን 2017 ዓ.ም. ጀምሮ በተከሰተው የጸጥታ ችግር የተፈናቀሉ በሺሕዎች የሚቆጠሩ ነዋሪዎች “አሁንም ያላስረከባችሁትን የጦር መሳሪያ አምጡ” የሚል ግፊት እየደረሰባቸው መሆኑን ማክሰኞ የካቲት 18 ቀን 2017 ዓ.ም. ባወጣው መግለጫ አመልክቷል። በዚሁ መግለጫ ላይ ከቀድሞ ቀያቸው ወደ ደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ክልል፣ ካፋ ዞን፣ ጊምቦ ወረዳ የተፈናቀሉት እነዚሁ ነዋሪዎች፣ በወረዳ አስተዳደሩ አማካይነት በትምህርት ቤቶችና ድንኳኖች ተጠልለው ድጋፍ እያገኙ መሆኑን ፓርቲው አስታውቋል።
ይሁንና “በዜጎች ግድያና ቤት የማቃጠል ወንጀሎች የተሳተፉ አካላት ላይ አስፈላጊው ማጣራት ተደርጎ ለፍርድ አለመቅረባቸው ችግሩን አባብሶታል” በማለት አጽንዖት የሰጠው እናት ፓርቲ፣ በአካባቢው ሰፍሮ የሚገኘው የመከላከያ ሰራዊት የማረጋጋት ስራ እንዲሰራና መንግስትም ቤታቸው ተቃጥሎባቸው በድንኳኖችና ትምሕርት ቤቶች የተጠለሉ ነዋሪዎች በአፋጣኝ መልሰው የሚቋቋሙበትን ሁኔታ እንዲያመቻች ጠይቋል።

የትግራይ ጊዜያዊ አስተዳደር ምክትል ፕሬዚዳንት እና የፀጥታ ዘርፍ ሃላፊ ሌተናል ጄኔራል ታደሰ ወረደ፤ በአሁኑ ወቅት ሁሉም የትግራይ ዞኖች ሁለት አስተዳዳሪዎች እንዳሏቸው ተናግረዋል። ምክትል ፕሬዚዳንቱ አክለውም፤ የጊዜያዊ አስተዳደሩ መንግስታዊ መዋቅር እንዳይፈርስ ጥንቃቄ ሊደረግ ይገባል፤ ብለዋል።
ማክሰኞ የካቲት 18 ቀን 2017 ዓ.ም. ከደቡብ ምስራቅ ትግራይ ዞን፣ ስምንት ያህል ወረዳዎች ከተውጣጡ ተወካዮች ጋር በመቐለ ሰማዕታት ሐውልት አዳራሽ ውይይት ያደረጉት ሌተናል ጄኔራል ታደሰ፤ በዞኖች፤ በወረዳዎችና በከተማ አስተዳደሮች አወቃቀር ዙሪያ አስተያየታቸውን ሰንዝረዋል። ከተወካዮቹም የተለያዩ ጥያቄዎችን ተቀብለዋል፡፡
ጊዜያዊ አስተዳደሩ የፕሪቶሪያ የሰላም ስምምነት የማስፈጸም አቅም እንደሌለውና ምዕራብ ትግራይ ጨምሮ ሌሎች ከጦርነቱ በፊት በትግራይ ክልል አስተዳደራዊ መዋቅር ስር “ነበሩ” የተባሉ አካባቢዎችን ወደ ቀድሞ አስተዳደራዊ መዋቅራቸው መመመለስ እንዳልቻለ ከተሰብሳቢዎቹ ተነግሯል። አያይዘውም፣ “በየወረዳ እና ቀበሌ ‘ቁጥር ሁለት’ የተባለ ማሕተም እየተበተነ ነው” ብለዋል።
ሌተናል ጄኔራል ማብራሪያቸውን ሲጀምሩ፣ “የወረዳ እና የከተማ አስተዳደር ምክር ቤቶችን በተመለከት የተነሳው ችግር በግልጽ የሚታወቅ ነው” ብለዋል። አክለውም፣ “የወረዳ አስተዳዳሪ እና የከተማ ከንቲባ የሚሾመው በምክር ቤት ነው። ከዚህ ውጪ አቋራጭ መንገድ የለም” በማለት አሳስበዋል።
“በደብዳቤም ሆነ በሌላ መልኩ የሚፈጸም ሹመት አይኖርም” ያሉት ሌተናል ጄኔራል ታደሰ፣ የከተማ እና ሌሎች የአስተዳደር መዋቅሮች በጊዜያዊ አስተዳደሩም ሆነ በሕዝባዊ ስብሰባ የሚቀያየሩ እንዳልሆኑ ተናግረዋል። ቀጥለውም፣ “ሕገ መንግስታዊ ስርዓቱን አክብረን መቀጠል አለብን” ሲሉ በማመልከት፣ ከማህተም ርክክብ፣ ከከንቲባ እና የወረዳ አስተዳዳሪ ሹመት ውዝግብ ጋር በተያያዘ ከመንግስት እና ከሌሎች ወታደራዊ አመራሮች ጋር በመተባበር ችግሩን ለመቅረፍ እየሰሩ መሆናቸውን ለተሰብሳቢዎቹ አስታውቀዋል።
በሁሉም የትግራይ ዞኖች ሁለት አስተዳዳሪዎች ስለመኖራቸው ያስረዱት ምክትል ፕሬዝዳንቱ፣ ለአብነት ያህል ምዕራባዊ፣ ሰሜን ምዕራብ፣ ምስራቅ፣ ደቡብ ምስራቅ እና ደቡብ ዞኖችን በመጥቀስ፣ ከንቲባ የሌላቸው ከተሞችም ጭምር መኖራቸውን ጠቅሰዋል። በተጨማሪም፣ የጊዜያዊ አስተዳደሩ መንግስታዊ መዋቅር እንዳይፈርስ ጥንቃቄ ሊደረግ እንደሚገባ አሳስበዋል።
ሌተናል ጄኔራል ታደሰ “ከእንግዲህ በወረዳዎች እና ዞኖች ከምክር ቤቶችም ሆነ ከአስተዳዳሪዎች ጋር በተያያዘ የሚፈጠር ግጭት አይፈጠርም” ሲሉ ለተሰብሳቢዎቹ ቃል ገብተዋል።
በሌላ በኩል፣ በጊዜያዊ አስተዳደሩ የተሾሙት የመቐለ ከተማ ከንቲባ ብርሃነ ገብረኢየሱስ ከከተማዋ ወጣቶች ጋር ማክሰኞ የካቲት 18 ቀን 2017 ዓ.ም. ውይይት አድርገው እንደነበር ለማወቅ ተችሏል። አቶ ብርሃነ “ህወሓት ለበርካታ ጊዜያት በተጠራቀሙ ችግሮች ተተብትቦ ወደ ፊት መራመድ ተስኖታል” በማለት ወቅሰዋል።
አቶ ብርሃነ አክለውም፣ “ፓርቲው ጠልፈው የጣሉትን ችግሮች ከመፍታት ይልቅ ማሰብ አቁሞ ሕዝቡን ወደ ከባድ ስቃይ አስገብቶታል” ሲሉ ተናግረዋል። “’ራሴን በራሴ አስተዳድራለሁ፤ የሚሆነኝን እመርጣለሁ’ ያለ ትግራዋይ ማንኛውም ጥቃት ሊደርስበት አይገባም” ያሉት አቶ ብርሃነ፣ “ከፌደራል መንግስት የሚያገናኘን የፕሪቶሪያ ውል ማደናቀፍ ማለት እንደሕዝብ አደጋ ላይ የሚጥል ነው” ብለዋል።  

አትሌት ሰለሞን ባረጋ በስፔን ሲቪያ በተደረገው የማራቶን ውድድር አሸንፏል፡፡
አትሌት ሰለሞን የማራቶን ውድድር ሲያደርግ ይህ የመጀመሪያው ሲሆን፤ 2 ሰዓት ከ5 ደቂቃ ከ14 ሰከንድ በመግባትም ውድድሩን ማሸነፍ ችሏል፡፡
በሌላ በኩል በሲቪያ በተደረገው የሴቶች የማራቶን ውድድር አትሌት አንችንአሉ ደሴ አሸንፋለች።
አትሌት አንችንአሉ ደሴ ርቀቱን 2፡22፡17 በሆነ ሰዓት በመግባት ውድድሩን በበላይነት ማጠናቀቋን የኢትዮጵያ አትሌቲክስ ፌዴሬሽን መረጃ አመልክቷል፡፡  

“ይህ በየቦታው ሊነገር የሚገባ ድንቅ ታሪክ ነው”


በልደታ ክፍለ ከተማ ወረዳ 10 የሚገኘውና በተለምዶ ዋንዛ ሰፈር እየተባለ ይጠራ የነበረው መንደር አሁን አዲስ ስያሜ አግኝቷል - ”የበጎነት“ መኖሪያ መንደር የሚል፡፡ ስያሜውን ያገኘው ደግሞ በከተማዋ በስፋት እየተለመደ በመጣው የበጎ ፈቃድ አገልግሎት፣ ቀና ልብ ባላቸው ባለሃብቶች በተገነቡ በርካታ መኖሪያ ቤቶች በመሞላቱና መኖሪያና መጠጊያ ያጡ አቅመ ደካሞች መጠለያ ያገኙበትና የዘመነ አኗኗር የጀመሩበት በመሆኑ ነው፡፡
በ2015 ዓ.ም በክረምት የበጎ ፍቃድ አገልግሎት ሲጀመር፣ የአዲስ አበባ ከተማ ከንቲባ ወይዘሮ አዳነች አቤቤ፣ ወደ ዋንዛ ሰፈር ጎራ ብለው ነበር፡፡ የነዋሪዎችን የኑሮ ሁኔታ ከጎበኙ በኋላም በአጭር ጊዜ ውስጥ ወደ ተሻለ የመኖሪያ ሥፍራ  እንደሚሸጋገሩ ቃል ገቡላቸው፡፡
በአዲስ አበባ ከተማ ከአገራዊ ለውጡ በኋላ ባህል እየሆነ በመጣው የበጎ ፍቃድ አገልግሎት የበርካታ ነዋሪዎች የኑሮ ጫና ተቃሏል፡፡ ነዋሪዎች ክብር ያለው ኑሮ ይገባቸዋል የሚል ጽኑ እምነት ያለው  የከተማ አስተዳደሩ፤ ዜጎች ከደቀቁና ለኑሮ ምቹ ካልሆኑ ቤቶች ወጥተው የተሟላ የመሰረተ ልማት ወዳላቸው ዘመናዊ ቤቶች እንዲሸጋገሩ ሲያደርግ ቆይቷል፡፡
ባለፈው ማክሰኞ የካቲት 11 ቀን 2017 ዓ.ም የአዲስ አበባ አስተዳደር ከሚድሮክ ኢንቨስትመንት ግሩፕ  ጋር በመተባበር በበጎነት መንደር የገነባቸው ሁለት ባለ 9 ወለል የመኖሪያ  ህንጻዎች ተጠናቀው በከንቲባ አዳነች አቤቤ የተመረቁ ሲሆን፤ መኖሪያ ቤቶቹም  ለነዋሪዎች ተላልፈዋል፡፡
በዚህ የመኖሪያ መንደር የእንጀራ ማእከል ህንፃ ተገንብቷል፣ የወንዶችና የሴቶች የውበት መጠበቂያ፤ ፀጉር ቤት፣ የልብስ ስፌት ማሽን ተሟልቶ ለአገልግሎት ዝግጁ ሆኗል፡፡ በተጨማሪም ለእናቶችና ለህፃናት አገልግሎት እንዲሆን ተቀናጅቶ የተሰራ የልማት ስራ ተካቶበታል፡፡ በእንጀራ ማእከሉ ያሉ እናቶች ከክፍለ ከተማው የተደራጁና ሰልጥነው ወደ ስራ የገቡ ናቸው፡፡
በፀጉር ቤቱ፣ በውበት መጠበቂያዎቹ፣ በህፃናት እንክብካቤዎችና በልብስ ስፌት ላይ የሚሰማሩት  የነገዋ ሴቶች ሰልጣኝ እህቶቻችን ናቸዉ፡፡
የመኖሪያ ቤቶቹ ተጠቃሚ የሆኑ ነዋሪዎች ቤታቸውን ከተረከቡና ገብተው ከጎበኙ በኋላ በሰጡት አስተያየት፤ በከተማ አስተዳደሩ የተሰጣቸው መኖሪያ ቤት ከግምታቸውና ከጠበቁት በላይ እንደሆነባቸው በመግለጽ፤ ምስጋናቸውን አቅርበዋል፡፡
አቶ ገብረመድህን አያሌው አካል ጉዳተኛ የአካባቢው ነዋሪ ሲሆኑ፤ የቀድሞ ቤታቸው ሊወድቅ የደረሰና ዝናብ የሚያስገባ እንደነበረ ይናገራሉ፡፡ ከሁሉም በላይ ደግሞ የመጸዳጃው ሩቅ መሆን ለእርሳቸው ዓይነት በዊልቼር ለሚጠቀም አካል ጉዳተኛ አስቸጋሪ እንደነበር ገልጸዋል፡፡ አሁን የተሰጣቸው መኖሪያ ቤት ግን በቃላት ከሚገልጹት በላይ ምቹና ያልጠበቁት እንደሆነባቸው ተናግረዋል፡፡  
“የበፊቱ መኖሪያ ቤት የግድ ሆኖ ነው እንጂ ለእንደ እኔ ያለው አካል ጉዳተኛ አመቺ አልነበረም፡፡  አሁን ዊልቼሩ ቤት ድረስ ገብቶ ሶፋ ላይ ቁጭ ያደርገኛል፡፡ ሁሉም ነገር ምቹ ሆኖልኛል” ብለዋል፤ አቶ ገብረመድህን፡፡ በቃላቸው መሰረት አዲስ መኖሪያ ቤት ገንብተው ለሰጧቸው ከንቲባ አዳነች አቤቤም፤ “የሥራ ጊዜያቸውን የተባረከ ያድርግላቸው” ሲሉ አመስግነዋል፡፡  
ሌላዋ በአዲሱ መኖሪያ ቤታቸው የተደሰቱት ወ/ሮ እልፍነሽ ሰንበቴ፤ “ከንቲባዋ በ3 ወር ውስጥ ቤት ሰርቼ እሰጣችኋለሁ ስትለኝ እንደዚህ ዓይነት ቤት ሰርታ የምትሰጠኝ አልመሰለኝም ነበር” ብለዋል፡፡ የቀድሞው ቤታቸው ምን ይመስል እንደነበር ሲናገሩም፤ “አስር ሆነን ነበር አንድ ቤት ውስጥ የምንኖረው፤ እኔ እግሬ ስለማይታጠፍልኝ መጸዳጃ ቤት ወንበር ተቀምጦልኝ ነበር የምጠቀመው” ያሉት ወ/ሮ እልፍነሽ፤ “ወደ አዲሱ ቤት ስገባ በደስታም በድንጋጤም እግሬ መሬት መርገጥ አቅቶት ነበር፡፡” ሲሉ የተፈጠረባቸውን ስሜት ገልጸዋል፡፡
የቀድሞ ቤታቸው በክረምት ሃይለኛ ጎርፍ የሚሄድበትና የሚቸገሩበት እንደነበር የሚናገሩት ሌላዋ የቤት ተጠቃሚ ወ/ሮ አረጋሽ ቱሉ፤ እንደዚህ ጽድት ያለ ራሱን የቻለ መኖሪያ ቤት ይሰጠናል ብለን አልጠበቅንም ነበር ብለዋል፡፡ ከበፊቱ የተሻለ ይሆናል ብለን ነው የጠበቅነው እንጂ በዚህ ደረጃ አልጠበቅንም ያሉት ወ/ሮ አረጋሽ፤”እግዚአብሄር ይመስገን የእጥፍ እጥፍ አድርገው ነው የሰጡን“ ሲሉ ጥልቅ ምስጋናቸውን አቅርበዋል፡፡
በበጎነት  መንደር የመኖሪያ ህንጻዎች የምርቃት ሥነስርዓት ላይ  ከንቲባ  አዳነች አቤቤ ባደረጉት ንግግር፤ “ይሄንን ለመሥራት ብዙ ርቀት መሄድ አላስፈለገንም፤ መንግሥት ቦታውንና አንዳንድ ተጨማሪ የሚላቸውን ግብአቶች በማቅረብ፣ ባለሃብቱ ደግሞ ገንዘቡን ይዞ በጋራ በመተባበር ለወገኖቻችን የሰራናቸው ቤቶች ናቸው” ብለዋል፡፡
 ልማታችን ሁሉንም በየደረጃው የሚያካትት እንዲሆንና ማህበራዊ ፍትህ እንዲነግስ እየተጋን ነው ያሉት   ከንቲባዋ፤ ይሄንን ደግሞ ብቻችንን በመንግሥት በጀት ብቻ ልንወጣው ስለማንችል እንደ ሚድሮክ ኢንቨስትመንት ግሩፕ ያሉትን የግል ተቋማት አስተባብረን እየሰራን እንገኛለን ብለዋል፡፡
“መንግሥት ካስተባበረ የሚተባበር ህዝብ አለ፤ ሚድሮክ ኢንቨስትመንት ግሩፕ ለዚህ ጥሩ  ማሳያ ነው” ሲሉም አክለዋል፤ ከንቲባ አዳነች አቤቤ፡፡ ሃምሳ ሎሚ ለአንድ ሰው ሸክሙ ለሃምሳ ሰው ጌጡ የሚለውን ብሂል የጠቀሱት ከንቲባዋ፤ ከተባበርን ሃብት አናጣም፤ ብዙ መሥራት እንችላለን፤ ብዙ ስንሰራ ደግሞ የብዙዎችን ህይወት እንለውጣለን፤ ብለዋል፡፡  
የሚድሮክ ኢንቨስትመንት ግሩፕ ዋና ሥራ አስፈጻሚ አቶ ጀማል አህመድ በበኩላቸው፤ የከተማ አስተዳደሩ የሰው ተኮር መርሃ ግብር፣ ባለሃብቱ ማህበራዊ ሃላፊነቱን በተገቢው መንገድ እንዲወጣ እያገዘው መሆኑን ገልጸዋል፡፡   
ለወገን ተብሎ የሚከናወን ተግባር በረከት እንጂ የሚያጎድል ነገር የለውም ያሉት ዋና ሥራ አስፈጻሚው አቶ ጀማል አህመድ፤ በዚህ እምነታችን የሚድሮክ ኢንቨስትመንት ግሩፕ 72ሺውም ሠራተኛ መግባባት ላይ ደርሶ፣ 10 ከመቶ ትርፋችንን በየክልሉ ለበጎ ተግባር እያዋልን እንገኛለን ብለዋል፡፡
በበጎነት መኖሪያ መንደር ምርቃት ላይ ተገኝተው ንግግር ያደረጉት በተባበሩት መንግሥታት ድርጅት የልማት ፕሮግራም (UNDP) የኢትዮጵያ ተጠሪ ዶ/ር ሳም ዱ፤ በዚህ እየተመለከትነው ባለው ተግባር እኔ በግሌ ከልብ ተነክቻለሁ ሲሉ የተሰማቸውን ስሜት ገልጸዋል፡፡
“ልማት ማለት የከበረ ጉዳይ ነው፤ ልማት ማለት የትብብር ጉዳይ ነው፤ ልማት ማለት ሰዎች ትርጉም ያለው ኑሮ እንዲኖሩ ማድረግ ነው” ያሉት ዶ/ር ሳም፤ አሁን ላይ በኢትዮጵያ አዲስ ታሪክ ማየት ጀምረናል ብለዋል፡፡
“ዩኤንዲፒ በኢትዮጵያ ለ10 ዓመታት ቆይቷል፤ አሁን ላይ ግን አዲስ ታሪክ ማየት ጀምረናል፡፡ የከተማ አስተዳደሩና የግሉ ዘርፍ ዝቅተኛ ኑሮ ያላቸውን ዜጎች ኑሮ ለማሻሻል በጋራ የሰሩትን ታሪክ እየተመለከትን ነው” ሲሉ አድናቆታቸውን ገልጸዋል፡፡
አክለውም ሲናገሩ፤“የግል ተቋማትና መንግሥት ለማህበራዊ ችግር የተጋለጡ ዜጎችን ህይወት ሲቀይሩ እየተመለከትን ነው፤ ይህ ለእኔ በየቦታው ሊነገር የሚገባ ድንቅ ታሪክ ነው፡፡” ብለዋል፤ ዶ/ር ሳም ዱ፡፡

ከአንገቱ በላይ… “በጥቀርሻ ጉም የተሸፈነው የቱርኪሚርክ ተራራ”… ያደፈጠ አውሬ ይመስላል። በድብቅ ሳይሆን በግላጭ ያደፈጠ። ጉሙ ቢገለጥና ጭንቅላቱ ቢታይ ደግሞ አስፈሪነቱ ይብስበታል ብለው ያስባሉ - የራቶስ ከተማ ነዋሪዎች። የተከፈተ አፍ ሊኖረው ይችላል። በጣም የሚያስጨንቃቸው ግን፣ ጭንቅላት ባይኖረውስ የሚለው ስጋት ነው።
ከተማዋ መፈናፈኛ እንዳታገኝ ዙርያዋን የከበበ የእስር ቤት ግንብ ነው - ተራራው። ከእግሩ ሥር ቁልቁል በአይነ ቁራኛ የሚጠባበቅ አውሬም ይመስላል። የከተማዋ ነዋሪዎች አሁንም አሁንም ቀና ብለው ሽቅብ ያዩታል። ሁሌም ስለተራራው ያስባሉ። በሕልማቸውም በውናቸው ከአእምሯቸው አይጠፋም። ግን ሐሳባቸውንና ቅዠታቸውን በግልጽ አያወሩም።
በጥቀርሻ ጉም ከተሸፈነው አናት በታች የዝገት ክምር የመሰለ መልክ አለው። ሲነሳበት ግን መልኩና ቀለሙ ይለዋወጣል። በቁጣ ይንቀጠቀጣል። ሬንጅ የመሰለ ጅራት ያወጣል፡ መርዛማ ጭስ እየለቀቀ በከተማዋ ላይ ብናኝ ያርከፈክፋል።
ዶይቃዊው ንጉሥ ከሥልጣኑ በተባረረበትና አገር ጥሎ በጠፋበት ጊዜ ነው የተራራው ባህርይ የተቀየረው ይላሉ - ገሚሶቹ። ተለዋዋጭ መልክና አመል ያመጣው በዚያችው ዕለት እንደሆነ ይተርካሉ። ታሪክ ተበላሸ ብለው የድሮውን ይናፍቃሉ። ያልሠራነው ገድል፣ ያልሮጥንበት ዳገት የለም ብለው ይናገራሉ። ታሪክ ሁሉ ተፈጽሞ የተጠናቀቀ፣ ከእንግዲህም ማሰብና መስራት የማያስፈልግ ይመስል።
ገሚሶቹ ግን ተራራው ከነ ባህርይው ድሮም የነበረ ነው ብለው ይተማመኑበታል። ተለዋዋጭነቱ ባይጨበጥላቸውም፣ በጥቀርሻ ጉም ቢያጨልምባቸውም፣ ይሻለናል ይሉለታል።
ሌሎች እንደሚተርኩት ከሆነ ግን፣ ከሌሎች ተራሮች የተለየ ባህርይ አልነበረውም። እንዲያውም አፈጣጠሩና ተለዋዋጭ አመሉ ድንገተኛ ክስተት ነው። ከዕለታት አንድ ቀን፣ በድንገት ንጉሡ ጠፋ፤ በድንገት ተራራው ተከሰተ - ከተለዋዋጭ አመል ጋር።
(የሌሊሳ ግርማ አዲስ የረዥም ልብወለድ ድርሰት በእንዲህ ዓይነት ትረካ ነው መጽሐፉን የሚጀምረው፡፡ ማራኪ የፋንታሲ ዘይቤ ነው፡፡ ግን ምናባዊ ዓለም ብቻ አይደለም፡፡ የዛሬ የዘመናችን የዚህችው የዓለማችን ገፅታና መንፈስ ለማሳየት የተወጠነ ድርሰት ነው፡፡)
በራቶስ ነዋሪዎች ዘንድ የተለያዩ ወሬዎችና የተምታቱ ሐሳቦች ቢበዙ ላይገርም ይችላል። የለውጥ ዘመን ላይ የሐሳቦች ግርግር ይፈጠራል። ሲያስለቅሱ የነበሩ አስጨፋሪ፣ ፊተኞችም ኋለኞች ይሆናሉ። የታችኞችም የበላይ። ተራራው ተንዶ ሜዳ ይሆናል፤ ሸለቆው አብጦ ተራራ ያክላል። የሐሳቦች መልክዓ ምድር ይለዋወጣል። ነገሮች በፍጥነት ይሾራሉ።
እንደ ጥንቱ ቢሆን፣ በለውጥ ምክንያት የሚከሰት ጊዜያዊ የሐሳቦች ግርግር፣ ውሎ አድሮ ይረጋጋል። መልክ ይይዛል። የዛሬው ዓለም ግን ከጥንቱ ይለያል። በመላው ዓለም የሚታየው የዘመናችን የሐሳቦች ግርግር፣ ጊዜያዊ የሽግሽግ ሆይሆይታ ወይም የሽግግር ሁካታ አይደለም።
አንድ የሐሳቦች ማዕቀፍ በብጥብጥ ደፍርሶ፣ ሌላ የተጣራና የተንጣለለ የሐሳቦች ማዕቀፍ አይፈጠርም። ነባሩ ተደፍቶ በቦታው ሌላ አዲስ ተተክቶ አያድርም። የፈራረሱት ጠጠሮች፣ የተበታተኑት ነጠብጣቦች እንደገና በአዲስ መንገድ እንዲሰባሰቡ፣ ሥርዓት እንዲይዙና ምስል እንዲፈጥሩ ማድረግ የሚችል ወይም የሚፈልግ የለም።
የጠጠሮች ክምችትና የነጠብጣቦች ትርምስ ነው የዘመናችን ግብ። ጠጠሮችን አዋቅሮ ወደ ቅርጽ ማድረስ፣ ነጠብጣቦችን አገናኝቶ ወደ መስመርና ወደ ምስል ማሸጋገር ድሮ ቀረ ተብሏል። ወይም እንደ ኋላቀርነት ተቆጥሯል።
ይህን የዘመናችንና የዓለማችንን መንፈስ ለመግለጽና ለማሳየት የሚሞክር ድርሰት ይመስላል - የሌሊሳ ግርማ ረዥም ልብወለድ መጽሐፍ።
“በታችም በምድር” በሚል ርዕስ ከሰሞኑ ለሕትመት የበቃው ድርሰት፣ የዘመናችንን የሐሳብ ግርግር በማሳየት ብቻ አይመለስም።
በሐሳቦች ግርግር በታመሰው ዓለም፣ የዓለማ አቅጣጫ በተምታታበት ቅብዝብዝ፣ በማንነት ቀውስ እየታመሰ ትርጉም ባጣ ሕይወት ውስጥ፣ ነጠብጣቦችን ሁሉ የሚጠቀልል ትልቅ ነጥብ የማግኘት ውጣ ውረድን ይተርካል - ድርሰቱ።
በኤሎምና በወላጆቹ ታሪክ።
ተወርዋሪ ኮከብ በመሰለው በኤሎምና በሃቴሉ የፍቅር ብልጭታ።
በተለይ ደግሞ በጠመዝማዛው የኤሎምና በአብነር ታሪክ።
እንደ ደቀ መዝሙርና እንደ መምህር ሆኖ የተጀመረው የኤሎምና የአብነር ታሪክ ወደ ሰማይ ለመምጠቅ ይምዘገዘጋል። የመምጠቂያ ጉልበቱ “እምነት” የተሰኘ ኃይል ነው። እየበረከተ እየበረታ የሚሄድ ኃይል ነው? ወይስ አላቂ ነዳጅ? ከምድር ከራቀ፣ ከዓለም ስበት ከተላቀቀስ ምን መተማመኛ ይኖረዋል?
እምነትን እያቀጣጠለ የሚምዘገዘገው የደቀ መዝሙርና የመምህር ግንኙነት፣ ሲብሰለሰል በቆየ ምክንያት ሳቢያ፣ ቁልቁል ገደል መግባት ይቀርለታል? ወደ ልዩነትና ወደ ተቀናቃኝነት ከመቀየር ይድናል?
ኤሎች የዘመናችንን የሐሳብ ግርግር አደብ ማስገዛት፣ ፍሬና ገለባውን ማጣራት፣ ትክክለኛ ሐሳቦችን በአንድ ማዕቀፍ መልክ ማስያዝ የሚቻለው፣ በሃይማኖት ወይም በእምነት አማካኝነት ነው ማለት ጀምሯል።
ዓለማ የጠፋበት አሰልቺ የመቅበዝበዝ ኑሯችን የሚፈወሰው፣ ዘላለማዊ እውነትን የምናገኘው እንዲሁም ዘላለማዊ የሥነምግባር መርህን የምንጨብጠው በሃይማኖት ነው የሚል ሆኗል እምነቱ።
ሕይወታችን ትርጉም የሚኖረው፣ ቅዠት ከመሰለው የማንነት ቀውስ የምንድነው፣ የሕይወትን ክብር ለማጣጣም የምንችለው፣ በእምነት እንደሆነ (የክብር አናት፣ የፍጽምና ጫፍ፣ የመልካምነት ከፍታን በማምለክ) እንደሆነም ያምናል። ይህን የማገኘው በሃይማኖት በእምነት ነው ይላል።
የሰው ልጅ በሐሳብ ግርግር የሚቃዠው፣ በዓላማ ቢስነት የሚቅበዘበዘው፣ ትርጉም ባጣ ሕይወት የሚባክነው… እምነትን በማጣት ነው እንደማለት ነው።
ለተበጣጠሱ ሐሳቦች አሰባሳቢ ማዕቀፍን፣ ለተበታተኑ የኑሮ እርምጃዎች የጉዞ መስመርን፣ ለተቃወሰ ማንነት ከውረደት ወደ ከፍታ የሚያመላክት የክብር ሰገነትን ማበጀት የግድ አስፈላጊ እንደሆነ መገንዘብና ለዚህም በጽናት መነሣት ትልቅ ቁምነገር ነው።
ሁሉንም ጉዳይ፣ ሁሉንም የሕይወት ገጽታ የሚያካትትና የሚያስተሳስር፣ ለሁሉም ሰው፣ በሁሉም ቦታና ጊዜ የሚያገለግል የሐሳቦች ማዕቀፍ ከሌለን፣ መውጫ በሌለው አዙሪት ቁልቁል እንወርዳለን፡፡ ሐሳባችንም፣ ኑሮና ተግባራችንም፣ የግል ባህሪያችንና መንፈሳችንም ሁሉ በቅዠት እየተዋጠ እንደሚሄድ የሚመሰክር ነው - የዘመናችን አዝማሚያ።
ነገር ግን፣ የዚህ ሁሉ ችግር መንሥኤ የሃይማኖት ወይም የእምነት እጦት ነው ወይ? ችግር የሚደርስብንስ ከእምነት ስለተራራቅን ነው ወይ?
መፍትሔውስ ራሳችንን ለእምነት ማስገዛት ብቻ ነው?
በእርግጥ እምነት መያዝና መጽናት ቀላል ነገር እንዳልሆነ በኤሎም ሕይወት ተተርኳል። ከቤተሰብና ከወዳዶች ጋር የመጣላት ፈተና ይመጣበታል። በሐሰት የሚወነጅሉና የሚያሳድዱ ይነሡበታል። የጠረጠሩት እርግጠኛ ሆነው ይመሰክሩበታል። ያመናቸው ይክዱታል።…
እምነት ለብዙ ችግር ይዳርጋል፤ ያመነ ፈተና ይበዛበታል ያስብላል - ነገሩ።
ግን ደግሞ፣ ችግርና ፈተና የሚበረታው እምነት በሌላቸው ሰዎች ላይ እንደሆነ፣ እምነት የችግሮች መፍትሔ እንደሆነም ይናገራል።
እምነት ችግሮችን ይጠራል ወይስ ችግሮችን ያባርራል? በሁለቱም አቅጣጫ የተምታቱ ሐሳቦችን እየያዘ ይሆን እንዴ?
በኤሎም ታሪክ ሲነሡ ካየናቸው ጥያቄዎች አንዱ ይሄ ነው፡፡ ግን ገና ብዙ አስቸጋሪ ጥያቄዎችንም ሸውዶ ማለፍ አይችልም፡፡
ከ40 በላይ ሃይማኖቶችን በያዘች ከተማ ውስጥ ነው የሚኖረው። እርስ በርስ “መናፍቅ” እየተባባሉ ይወጋገዛሉ።
የትኛው ሃይማኖት ወይም የትኛው እምነት ነው ትክክል?
የሱ እምነት ከሌሎቹ እምነቶች በምን ይበልጣል?
ማስረጃ ልዘርዝር፤ ማረጋገጫ ላቅርብ ካለ… ጉዳዩ የዕውቀት ጉዳይ ይሆናል። ትልቁ ማዕቀፍ ሃይማኖት ወይም እምነት ሳይሆን፣ በማስረጃ የተረጋገጠ ዕውቀት ነው ወደ ማለት ያመራል።
ማስረጃና ማረጋገጫ አያስፈልገኝም፤ የኔ እምነት ከሌሎች እምነቶች እንደሚበልጡ “አምናለሁ”… የሚል ከሆነ ደግሞ… ከሌሎች እምነቶች ጋር ተመሳሳይ ይሆናል። ሌሎች ሰዎችም ለእምነታቸው ማስረጃና ማረጋገጫ እንደማያሻቸው ይናገራሉ። “የኔ እምነት ከሌሎች እንደሚበልጥ አምናለሁ” እያሉ ነው እርስ በርስ የሚወጋገዙት፤ የሚዘምቱት። ቢያንስ ቢያንስ፣ መናፍቅ ወይም ከሃዲ እያሉ ይሰዳደባሉ።
የኤሎም መንገድ ከነዚሁ ማህበር የተለየና የተሻለ መሆኑን እንዴት ማሳየት ይችላል?
እምነቱ በሚያመጣው ፍሬ? የኤሎምና የተቀናቃኙን ፉክክር በማነጻጸር ይሆን የእምነቱን ትክክለኛነት ማረጋገጥ የሚቻለው?
የኤሎም ፈተና ይህ ብቻ አይደለም። በየአቅጣጫው ከእልፍ ሰዎች አእምሮ እንደ አሸን እየተፈለፈሉ የሚያድሩና አገር ምድሩን የሚያጥለቀልቁ የዓመጽ ሐሳቦችን ማበጠርና ለማዕቀፍ ማስገዛት፣ አገር ምድሩን የሚያዳርሱ የዓመጽ ሤራዎችንና ጥፋቶችን ማሸነፍ ይችላል ወይ? ካልቻለ ፍሬው ምኑ ላይ ነው?
በተለዋዋጭ ዓመል ከተማዋን ከሚያስጨንቃት ከግዙፉ ተራራ ጋር እንደመፋለም ነው - ፈተናው።
ጭንቅላት ይኑረው አይኑረው የማይታወቅ የዘመናችን ተለዋዋጭ የሐሳብ ግርግርን በሃይማኖታዊ እምነት ማሸነፍ እንደማለት ነው።
ከአንገት በላይ በጥቀርሻ ጉም የተሸፈነ፣ መርዛማ ጭስ እየተፋ ብናኙን የሚያርከፈክፍ፣ መልክና ቀለሙን የሚለዋውጥ፣ አገሬውን የከበበ አውሬ ወይም የዝገት ክምር የመሰለ ግዙፍ አመለኛ ተራራ ነው የዘመናችን የሐሳብና የመንፈስ ግርግር።
እና በቅንጣት እምነት ተራራውን “ወግድ” ብሎ መናድና ማባረር ይቻላል?
ድርሰቱን ብታነብቡና ብንነጋገርበት መልካም ይመስለኛል።
አቀራረቡና አጻጻፉ ለንባብ የተመቸ ነው። ትኩረትን በየሚስቡና በሚያስደንቁ ገጸ ባሕርያት የበለጸገ ነው።
ከሁሉም በላይ ግን የዘመናችንን የሐሳብና የመንፈስ ግርግርን ለማሳየት፣ በዚሁ የትርምስ ዓለም ውስጥ የነባር ትውልድና የአዲስ ትውልድ ሕይወት ምን እንደሚመስል ለማስቃኘት የሚሞክር ድርሰት ነው።
የመዳኛው መንገድ የኤሎም እምነት ነው ከማለት ጎን ለጎን፣ የፕሮቴስታንት የመሰለ ሃይማኖት ነው መፍትሔው የሚልም ይመስላል።
እንዲህ ከማለት ግን፣ የእምነት አዳኝነት ወይም የሃይማኖት መፍትሔነት ላይ ያተኮረ ድርሰት ቢባል ይሻላል። ግን በትረካው ላይ የምናየው እምነት፣ የእውነት አዳኝ ነው ወይ? የምር መፍትሔስ ነው ወይ?


Page 5 of 760